በክለሳ ላይ ያለው የግቢ ጉባኤያት ሥርዓተ ትምህርት ትግበራው በ2004 ዓ.ም ይጀመራል ተባለ፡፡

 ዲ/ን ቴዎድሮስ ኃይሉ
 
ከ2000 ዓ.ም ጀምሮ እየተከናወነ ያለውን የግቢ ጉባኤያት የሥርዓተ ትምህርት ክለሳ በተመለከተ ከማዕከላትና ግቢ ጉባኤያት ተወካዮች ጋር ውይይት ተደረገ፡፡ ሥርዓተ ትምህርቱም ከ2004 ዓ.ም ጀምሮ ተግባራዊ እንደሚደረግ በማኅበረ ቅዱሳን የትምህርትና ሐዋረያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል አስታወቀ፡፡

ከግንቦት 26 እስከ ግንቦት 27 ቀን 2003 ዓ.ም በተደረገው የውይይትና የምክክር መርሐ ግብር ከ11 ማዕከላት የመጡ የትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ክፍል ኃላፊዎችና ከ15 ግቢ ጉባኤያት የተወከሉ ተማሪዎች የተሳተፉ ሲሆን ተወካዮቹ ከዚህ በፊት ይነሡ የነበሩ ችግሮች በክለሳውና በዳሰሳ ጥናቱ መታየቱ እንዳስደሰታቸው ገልጸው ለተግባራዊነቱ መፋጠን ይኖርብናል ሲሉ አስተያየት ሰጥተዋል፡፡
የክፍሉ አስተባባሪ ቀሲስ ታደሰ ጌታሁን እንደገለጡት ክለሳው የተሠራው በ2000 ዓ.ም የተካሄደውን የዳሰሳ ጥናት መሠረት በማድረግ መሆኑን ገልጸው፣ ይህም የዳሰሣ ጥናት ለግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች፣ ለመምህራን ለክፍሉ አባላት መጠይቆችን በመበተን፣ ቃለ መጠይቅ በማድረግ፣ በአካል ቅኝት በማድረግና በመሳሰሉት እንደተከናወነ አስታውቀዋል፡፡
እስከ አሁን ሲተገበር የነበረው ሥርዓተ ትምህርት ለማኅበሩ የመጀመሪያ በመሆኑ ወጥነትና አንዳንድ መሟላት ያለባቸው ነገሮች ሳይሟሉ ተግባራዊ እንደሆነ የገለጹት አስተባባሪው አሁን እየተከለሰ ባለው ግን አንድ ሥርዓተ ትምህርት ሊያሟላ የሚገባውን አሟልቷል ብለን እናምናለን፡፡ ማኅበሩም ለግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ምን ዓይነት ፍልስፍና መከተል አለበት የሚለው ግንዛቤ ውስጥ ገብቷል፡፡ በተለይም ወደ ግቢ ጉባኤያት እየገባ ካለው ትውልድ አንጻር ሥርዓተ ትምህርቱ ሰፊ ፍተሻ እንደተደረገበትና ለሙከራም ከሚቀጥለው ዓመት ጀምሮ እንደሚተገበር አጽንኦት ሰጥተው ተናግረዋል፡፡
ማኅበረ ቅዱሳን ከ1996 ዓ.ም ጀምሮ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ለሚያስተምራቸው የገቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ሥርዓተ ትምህርት በመቅረጽ 20 መማሪያ መጻሕፍትን በማዘጋጀት እያስተማረ እንደሚገኝ ቀሲስ ታደሰ አስታውሰው በሚሰጡ ትምህርቶች ድግግሞሽና መሳሳብ እንደሚስተዋል፣ ለትምህርቶቹ የተመደበላቸው ሰዓቶች ከሚሰጡት ትምህርቶች አንጻር የማይመጣጠኑ እንደነበር በዳሰሳ ጥናቱ ወቅት እንደችግር ጎልተው እንደታዩ ጠቅሰዋል፡፡ ከክለሳው በኋላ የነበሩት 20 ትምህርቶችም ወደ 8 ዝቅ ማለታቸውን ያወሱት ቀሲስ ታደሰ በተጨማሪም ሦስት አዳዲስ ትምህርቶች ታክለዋል፡፡ እነዚህም ትምህርተ ክርስትና መግቢያ፣ ትምህርተ አበውና ልሳነ ግዕዝ እንደሆኑ ገልጸዋል፡፡
ለግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች የሚሰጡ የትምህርት ዓይነቶችም ተማሪዎቹ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የቆይታ ጊዜያቸው የሚወሰን ሲሆን ለእያንዳንዱ ትምህርት ተመጣጣኝ ሰዓት፣ መለያ ቁጥር፣ ቅደም ተከተል እንዲሁም የትኛው የትምህርት ዓይነት ለማን ይሰጥ የሚሉ ጉዳዮች በቀጣይ የሚወሰኑ ናቸው፡፡
በሥርዓተ ትምህርቱ ክለሳ ፕሮጀክት መሠረት አዲሱ ሥርዓተ ትምህርት በዚህ ዓመት ተግባራዊ መሆን አልነበረበትም ወይ? ተብለው የተጠየቁት ቀሲስ ታደሰ ሲመልሱ ፕሮጀክቱ ከተጠበቀው በላይ ጊዜ የሚጠይቅ መሆኑንና በክለሳው የተሳተፉት ባለሙያዎች በሥራ መደራረብ ምክንያት ወደ ትግበራ መግባት እንዳልተቻለ ተናግረዋል፡፡ ቢሆንም ግን በ2004 ዓ.ም በተመረጡ ግቢ ጉባኤያት የሙከራ ትግበራ እንደሚጀመር አሳውቀዋል፡፡
ይህንን ሥርዓተ ትምህርት ከግብ ለማድረስ የግቢ ጉባኤያትና የማዕከላት ሥራ አስፈጻሚ አካላትን ግንዛቤ ማስጨበጥ እንዲሁም በቂ መምህራንን ለማፍራት ሥራ እየተሠራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
አስተባባሪው እንዳሉት ከሥርዓተ ትምህርት ጋር ተዛማጅ ሙያ ያላቸው አባላት ክለሳውን አጠናቆ ትግበራ ለመጀመር እንዲያስችል በትምህርትና ሐዋረያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል በመገኘት በሙያቸው ተሳትፎ እንዲያደርጉ ጠይቀዋል፡፡
ማኅበረ ቅዱሳን በቅዱስ ሲኖዶስ በጸደቀለት መተዳደሪያ ደንብ መሠረት ለግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ሥርዓተ ትምህርት ቀርጾ ተግባራዊ ካደረገ 7 ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ ይህ ሥርዓተ ትምህርት ከተተገበረ ከ4 ዓመት በኋላ የዳሰሳ ጥናት በማድረግ የማኅበሩ ሥራ አስፈጻሚ ጉባኤ 7 አባላት ያሉት ኃይለ ግብር አቋቁሞ ከ2001 ዓ.ም ጀምሮ የክለሳ ሥራው እየተከናወነ ይገኛል፡፡ 
hawire_Hiwot2.jpg

ከ 3000 በላይ ምዕመናን ይሳተፉበታል ተብሎ የሚጠበቅ መንፈሳዊ ጉዞ ተዘጋጀ

በተ/ሥላሴ ፀጋ ኪሮስ

ሰኔ 15 ቀን 2003 ዓ.ም

ከ6 ወራት በፊት ተዘጋጅቶ እንደነበረው በርካታ ምእመናን የሚሳተፉበት መንፈሳዊ ጉዞ ተዘጋጀ፡፡ ሐዊረ ሕይወት ቁጥር 2 የሚል ስያሜ ያለው ይህ ጉዞ ሰኔ 19 ቀን 2003 ዓ.ም ይከናወናል፡፡

hawire_Hiwot2.jpg

ከአዲስ አበባ 108 ኪ.ሜ ርቆ ፍቼ ከተማ ወደ ሚገኘው መካነ ሰማዕት አቡነ ጴጥሮስ ገዳም የሚደረገው ይህ ጉዞ መንፈሳዊ ሕይወታችን የምናጠነክርበት ይህም ከሆነ ዘንድ በቤተ ክርስቲያን የእኛ ድርሻ ምንድን ነው? ብለን ራሳችንን እንድንጠይቅና ኃላፊነታችንን እንድንወጣ የሚያስችል እንደሆነ የጉዞው አስተባባሪ ቀሲስ አንተነህ ጌጡ ተናግረዋል፡፡

ሐዊረ ሕይወት ምእመናን ከመኖሪያና ከሥራ ቦታቸው ራቅ ብለው በተሰበሰበ ልቡና የቅዱሳን ሰማዕታትና የጻድቃን በረከት በሚገኝበት ቦታ ተረጋግቶ ራስን እንዲያዩ የሚያስችል፣ የአበውን ተጋድሎ በመመልከትና በማስታወስ ከፍ ወደ አለ ሥነ ልቡና የሚያደርስና የቤተ ክርስቲያንን ጣዕም የሚያሳይ መንፈሳዊ ጉዞ እንዲሆን ታስቦ እየተዘጋጀ እንደሆነ በአስተባባሪዎቹ ተያይዞ ተገልጿል፡፡

በኢትዮጵያ አንድና ብቸኛ ወደ ሆነው የአቡነ ጴጥሮስ ገዳም በሚደረገው ጉዞ በሐዊረ ሕይወት ቁጥር አንድ ጉዞ ወቅት ተነስተው ላልተመለሱና አሁንም ለሚነሱ ጥያቄዎች ሰፋ ባለ ሁኔታ በአበው ሊቃውንት መልስ የሚሰጥበት የምክረ አበውን ዝግጅት በድጋሚ አካቷል፡፡ ባለፈው ከነበሩ መምህራንና ሊቃውንት በተጨማሪም ሌሎች በርካታ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን የሚገኙበት እንደሆነ ተገልጿል፡፡ በተለይም ይህ ጉዞ የቤተ ክርስቲያንን ችግር ተረድተን መፍትሔ ፍለጋ ለመሄድ አቅጣጫ የሚሰጥ እንደሆነ አጽንኦት ተሰጥቶበታል፡፡

“ገዳሙ አንድና ብቸኛ መሆኑና ከአካባቢው ምእመናን በስተቀር በብዙው ኅብረተሰብ ዘንድ አይታወቅም በአሁኑ ጉዞ ወደ 3000 ምእመናን ይዘን እንጓዛለን ብለን እናስባለን” ያሉት ቀሲስ አንተነህ የሄዱት ምእመናን ለሌሎች ስለሚያስተላልፉ ገዳሙን በቀላሉ ማስተዋወቅ ይቻላል፡፡ በዚህም ምዕመናን የራሳቸውን አስተዋጽኦ ለገዳሙ እንዲያበረክቱ ያደርጋል ሲሉ ሌላኛውን አላማ ተናግረዋል፡፡

ሰማዕቱ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ሊቀ ጳጳስ ዘምሥራቅ ኢትዮጵያ የኢጣሊያ ጦር ሀገራችን ኢትዮጵያን በወረረበት ወቅት አርበኞችን በማስተባበር በጀግንነት ያዋጉ ሲሆን በጦርነቱ መሃል ተይዘው ስለሃይማኖታቸው በመመስከር የሀገራቸውን መሬትም ለፋሽስት እንዳትገዛ በመገዘት ሐምሌ 22 ቀን 1928 በሰማዕትነት ያረፉ አባት ናቸው፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በ2001 ዓ.ም በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ የቅድስና ማዕረግ ሰጥታ ጽላት ተቀርጾላቸው እንዲሁም በስማቸው ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን በትውልድ ሀገራቸው ሰርታ ሰማዕተ ጽድቅ ዘኢትዮጵያ እያለች ታከብራቸዋልች፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ለምዕመናን መንፈሳዊ ሕይወት መጠንከር ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን የጠበቁ የተለያዩ መንፈስዊ ጉዞዎችን እንደሚያዘጋጁ የገለፁት ቀሲስ አንተነህ በቅርብ ጊዜ የአዲስ አበባ ማዕከል ባዘጋጀው መንፈሳዊ ጉዞ ከ3000 በላይ ምእመናንን የማኅበረሩን አባላት ሌሎች ማኅበራችንና ሰንበት ትምህርት ቤቶችን ይዞ ወደ ደብር ቅዱስ ደብር ጽጌ ማርያም ገዳም ያደረገውን የሐዊረ ሕይወት ቁጥር አንድ ጉዞን ተጠቃሽ አድርገዋል፡፡

የግቢ ጉባኤያትን ተማሪዎች መንፈሳዊ ሕይወት ለማሳደግ የሚያስችል የንሰሐ አባቶች ሴሚናር ተካሔደ

በእንዳለ ደጀኔ

ሰኔ 10 ቀን 2003 ዓ.ም 

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን በሰንበት ት/ቤቶች ማ/መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎችን መንፈሳዊ ህይወት ለማሳደግ የሚያስችል የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች የንስሐ አባቶች ሴሚናር ተካሔደ፡፡
ከግንቦት 24 እስከ ግንቦት 26 ቀን 2003 ዓ.ም አዲስ አበባ ላይ በተካሔደው የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች የንሰሐ አባቶች ሴሚናር በመላ ሀገሪቱ የሚገኙ ግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች የንስሐ አባቶች ተወካዮች የተሳተፉ ሲሆን፥ በሴሚናሩም በቤተክርስቲያን ወቅታዊ ሁኔታ የንስሐ አባቶች ሚና፣ ለግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች መንፈሳዊ እድገት የንስሐ አባቶች ሚና፣ ሉአላዊነት ዘመናዊነት በተለይ ከአንቀጸ ንስሐ አንፃር፣ የግብጽ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ተሞክሮ ወጣቶችን ለቤተክርስቲያን አገልግሎት ከማዘጋጀት አንፃር እና የማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎት ግቢ ጉባኤያትን ለቤተክርስቲያን አገልግሎት ከማዘጋጀት አንፃር የሚሉ ርዕሰ ጉዳዮችን መሠረት ያደረገ ነበር፡፡

ለመጀመሪያ ጊዜ በተዘጋጀው በዚህ የግቢ ጉባኤያት የንስሐ አባቶች ሴሚናር ቁጥራቸው 50 የሚደርሱ አባቶች መሳተፋቸው ታውቋል፡፡

በካህናቱ አቀባበል ላይ የተገኝተው መልዕክት ያስተላለፉት የማኅበሩ ሰብሳቢ ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ስዩም «እናንተን አባቶች እዚህ ድረስ እንድትመጡ ያስቸገርነው በግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች አገልግሎት ያላችሁ ድርሻ ታላቅ በመሆኑ ነው» ብለዋል፡፡

በሴሚናሩ ላይም ብፁዕ አቡነ ዮናስ የአፋር ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ እና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ተገኝተው ቡራኬና ቃል ምዕዳን የሰጡ ሲሆን «ማኅበሩ የሚያደርገው የልጅነት ድርሻውን በማገዝ እናንተ ካህናት ትልቁን ድርሻ ትይዛላችሁ» ብለዋል፡፡

ለ3 ቀናት በተካሔደው በዚህ ሴሚናር «እጅግ በጣም ተደስተናል» ያሉት ተሳታፊ ካህናቱ «ቀጣዩን ትውልዱ በመቅረጽና ለሀገርና ለቤተክርስቲያን ብቁና በሥነ-ምግባር የታነፁ ለማድረግ የምንችልበትን ግንዛቤ አግኝተናል። ይህም ካህናት ባገኘነው ግንዛቤና ልምድ ተነሳስተን ውጤታማ ሥራዎችን እንሰራለን» ብለዋል፡፡

ሴሚናሩም ሊቃውንቱን እርስ በእርስ ያስተዋወቀና በመረጃም ረገድ ልምድ ለመለዋወጥ መነሳሳትን እንደፈጠረላቸው ለማወቅ ተችሏል፡፡

hohitebirhan.jpg

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የተሐድሶ እንቅስቃሴ አለን? ዓላማውና ስልቱስ ምንድን ነው?

ሰኔ 11 ቀን 2003 ዓ.ም

/ምንጭ፦ ስምዐ ጽድቅ ልዩ እትም ግንቦት 2003 ዓ.ም/

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን “መታደስ አለባት” የሚሉ ድምፆችን የሚያሰሙ አካላት አሳባቸውን በተለያዩ መንገዶች ማሰማት ከጀመሩ ውለው አድረዋል፡፡ እነዚህ አካላት በመጽሔቶች፣ በጋዜጦች፣ በመጻሕፍት፣ በበራሪ ወረቀቶች፣ በዓውደ ምሕረት ስብከቶችና በሚያገኟቸው አጋጣሚዎች ሁሉ ይኸን ጩኸታቸውን ማስተጋባቱን ተያይዘውታል፡፡ እንዲህ እያሉ ያሉትም “ኦርቶዶክሳውያን ነን” እያሉ በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ በተለያየ ቦታና ሓላፊነት ላይ ካሉና እንጀራዋን ከሚበሉ፣ ጥቂቶች እንዲሁም ደግሞ በኅቡእና በግልጽ በተለያየ መልክና ቅርጽ ራሳቸውን አደራጅተው ቤተ ክርስቲያኗ ሳትወክላቸው እርሷን ወክለው፣ “እኛም ኦርቶዶክስ ነን” በሚል ካባ ራሳቸውን ደብቀው እምነቷንና ሥርዓቷን “ይህ ሳይሆን ሌላ ነበር” እያሉ ፕሮቴስታንታዊ ትምህርትና መንፈስ የተዋረሳቸው ሰዎች ናቸው፡፡

 
ተሐድሶ የሚባል ነገር አለን? እነዚህ አካላት በአንድ በኩል ተሐድሶ የሚባል ነገር እንደሌለና ተሐድሶ የሚባለው ጉዳይ የሆነ አካል (እነርሱ እንደሚሉት ማኅበረ ቅዱሳን) ስም ለማጥፋት ሲል የፈጠረው የፈጠራ ወሬ እንጂ በሕይወት የሌለ ምናባዊ ነገር እንደሆነ ያስወራሉ፣ ይናገራሉ፡፡ ግን በእውነት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ዶግማዋ፣ ቀኖናዋና ትውፊቷ መታደስ አለበት በማለት የሚሠራ የተሐድሶ እቅስቃሴ የለምን?

ይህን ጉዳይ እነርሱው በይፋ ካወጧቸው የኅትመት ውጤቶቻቸው ለመመልከትና ለመታዘብ ይረዳ ዘንድ ራሳቸው በተለያዩ መጻሕፍቶቻቸው፣ መጽሔቶቻቸውና ጋዜጦቻቸው ካወጧቸው መካከል የተወሰኑትን ብቻ እንመልከት፡-

hohitebirhan.jpg

“እንደ እውነቱ ከሆነ በወንጌል እውነት ከታደሱ በኋላ በየጊዜው እየተመዘዙ የወጡት ምእመናኖቿና አገልጋዮቿ በውስጧ ቆይተው የተሐድሶን ሥራ እንዲሠሩ ቢደረግ ኖሮ፣ በወንጌል ተሐድሶ ያገኙ ክርስቲያኖች ለዓመታት የጸለዩበትንና የጓጉለትን የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ተሐድሶ በቅርብ ጊዜ ሊያዩ ይችሉ እንደ ነበር የሚያምኑ ጥቂቶች አይደሉም፡፡” (ኆኅተ ብርሃን፣ መጋቢት 2002፣ ገጽ 15)

 


“ተሐድሶ እንቅስቃሴ በመሆኑ፣ እንቅስቃሴም ውጤታማና ትርፋማ ይሆን ዘንድ ዓላማን፣ ሒደትንና ግብን የያዘ ድርጊት እየተከናወነበት ያለ ሊሆን ስለሚገባው፣ ያለፈውና እየሆነ ያለው ግብረ ተሐድሶ ተመዝግቦ ለአሁኑና ለሚመጣው ትውልድ በሥነ ጽሑፍ ዳብሮና አምሮ ሊቀርብለት ይገባዋል፡፡” (ኆኅተ ብርሃን፣ መጋቢት2002፣ ገጽ 17) “በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ገብተን አረሞችን በገሀድ ካልነቀልን ተሐድሶን እንዴት ልናመጣ እንችላለን? መባሉ አይቀርም፡፡ ዳሩ ግን ስሕተቶችን ፊትለፊት ሳይቃወሙ ስሕተቶች እንዲታረሙ ማድረግ የሚቻልባቸው የተፈተኑ መንገዶች አሉ፡፡ ለምሳሌም …” (ኆኅተ ብርሃን፣መጋቢት 2002፣ ገጽ 19)

metkie.jpg


“ከ2000 ዘመናት በላይ ያስቆጠረች የእኛ ቤተ ክርስቲያንማ እንዴት አብልጦ ተሐድሶ (መታደስ) አያስፈልጋት?” (መጥቅእ፣ ኅዳር 2002፣ ገጽ 15) “ቤተ ክርስቲያናችን በክፉ ሰዎች ሴራ ዓላማዋን ስታለች፣ የሐዋርያትንም ትምህርት ገፍታለች፣ ስለ ሆነም ይህን የሐዋርያት ትምህርት በክፉዎች ምክንያት በመጣሱ በድፍረት ተሳስተሻልና ታረሚ ልንላት፣ በድፍረትም በሥልጣንም ሕዝቡን ልናስተምር ይገባል፡፡” (መጥቅእ፣ ኅዳር 2002፣ ገጽ 20) “ቤተ ክርስቲያናችን በየሀገሩ የተነሣውን የተሐድሶ የወንጌል እሳት በተለይ በሐረር፣ በባሕር ዳር፣ በአዲስ አበባ፣ በማርቆስ፣ በጎንደር፣ በሰሜን ሸዋ፣ በወሎ፣ በትግራይ፣ በባሌ ለማዳፈን ያን ሁሉ እልፍ አእላፍ ሠራዊት የቤተ ክርስቲያን አለኝታ ወጣት ወንጌል ባልገባቸው ምእመናንና ካህናት እያስደበደበች ለሌላ ድርጅት አሳልፋ ከመስጠት ይልቅ ስሕተቷን አርማ ልጆቿን በጉያዋ ብትይዝ ኖሮ ዛሬም ጭምር ጋብ ላላለው ፍጥጫ አትዳረግም ነበር፡፡” (መጥቅእ፣ ኅዳር 2002፣ ገጽ 16) “ሕዝባችን በልማድና በባህል ሃይማኖትን መያዙና ይህን የያዘውን ሃይማኖት ለመጣልና ለማጣራትም በቂ እውቀት ስለሚጎድለው በራሱ አንብቦ መረዳት ስለማይችል …” (የሚያሳውቁት ሃይማኖትን ለማስጣል ነው ማለት ነው) (ይነጋል፣ 1997፣ ገጽ 144)

 


እነዚህ እነርሱው ከጻፏቸውና አሳትመው ካሰራጯቸው መካከል ለአብነት ያህል የተጠቀሱት በግልጽ የሚያሳዩን ነገር ቢኖር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን እምነትና ትምህርት የሚቃወሙና ሊለወጥ ይገባል የሚሉ ራሳቸውን “ተሐድሶ” የሚል ስያሜ ሰጥተው በተለየ መልክና ቅርጽ በግልጽና በኅቡእ እየሠሩ ያሉ አካላት መኖራቸውን ነው፡፡ ራሳቸው እንዲህ በይፋ “እኛ አለን፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስ ቲያን ተሐድሶ ያስፈልጋታል” እያሉ እየተናገሩ “አይ፣ ተሐድሶ የሚባል ነገር የለም” ማለት እንዴት ይቻላል?

ዓላማቸው ምንድን ነው? ተሐድሶዎች ዋና ዓላማቸው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ዶግማ፣ ቀኖናና ትውፊት በመለወጥ ፕሮቴስታንታዊ ይዘት እንዲኖረው ማድረግ ነው፡፡ ምእራባውያን ሚሲዮናውያን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን አጥፍቶ ፕሮቴስታንታዊ ለማድረግ መሥራት ከጀመሩበት ከሃያኛው መቶ ዓመት መጀመሪያ አንሥቶ እስከ አሁን ድረስ ሦስት ስልቶችን ተጠቅመዋል፡፡ የመጀመሪያው እስከ 1950 ዓ.ም ድረስ የሠሩበት ስልት ሲሆን እርሱም የራሳቸውን አስተምህሮ ማስተማር ነበር፡፡

ከ1950 ዓመት ጀምሮ እስከ 1990 ዓ.ም ድረስ ደግሞ የሠሩት የራሳቸውን እምነት መሰበክ ሳይሆን በዋናነት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን በመንቀፍና በማጥላላት ምእመኑ እንዲኮበልል በማድረግ ነበር፡፡

ከ1990 ዓ.ም ጀምሮ እስከ አሁን እየሠሩበት ያለው ሦስተኛው ስልት ደግሞ "ኦርቶዶክስ ነኝ" ብሎ ውስጧ ገብቶ “ትታደስ” እያሉ በመጮኽ ቤተ ክርስቲያኗ እንዳለች እንድትለወጥ በማድረግ ምእመናኗን ከእነ ሕንፃዋና አስተዳደራዊ መዋቅሯ መረከብ ነው፡፡ የእነርሱ ምኞትና እቅድ የኢትዮጵያን ቤተክርስቲያን ወደ ሦስተኛው ሺሕ እንዳትሻገር ማድረግ ነበር፡፡ ነገር ግን እንዳሰቡት አልሆነም፡፡ በዚህም ብስጭታቸውን በተለያዩ ሚዲያዎች ገልጸዋል፡፡ ለምሳሌም ፓውልባሊስኪ (Paul Balisky) የተባለ “የዓለም አቀፍ ተልእኮ ማኅበር” የኢትዮጵያ ዳይሬክተር በ1992 ዓ.ም በወጣው “የክርስቲያን ሳይንስ ሞኒተር” በተባለ መጽሔት በሰጠው ቃለ መጠይቅ የደከሙት ድካምና ያወጡት ገንዘብ ሁሉ ወደ ጠበቁት ግብ እንዳላደረሳቸው፡-

“ይህ ሁሉ ጥረት ቢደረግም ወንጌላውያኑ አሁን በማደግ ላይና በመካከለኛ ኑሮ ላይ ያለውን የከተማውን ኅብረተሰብ መቀየር አልቻሉም፡፡ ምክንያቱም የተማረና ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል ከፍተኛ ቅንዓት ያለው የወጣቶች ኃይል ማኅበረ ቅዱሳን የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን በሃያ አንደኛው መ/ክ/ዘመን ዘልቃ መጓዝ ትችል ዘንድ እየተጋደለ ነውና፡፡” በማለት ከሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን በፊት የማጥፋት ሕልም እንደነበራቸው ገልጸዋል፡፡(The Christian Science Monitor, 8 June, 2000)

ስለሆነም ከዚያ በፊት ያደርጉት እንደነበረው በውጭ ሆኖ ምእመናንን ለመንጠቅ በመሥራት ብቻ ካሰቡት ቤተ ክርስቲያኒቱን ሙሉ በሙሉ የማጥፋት ግብ ለመድረስ ቀላል እንዳልሆነ ተረዱ፡፡ ስለዚህ አዲስ ስልት መቀየስ አስፈለጋቸው፡፡ ይህም “እናድሳለን”

በሚል ሽፋን ከውጭ ወደ ውስጥ ሠርጎ በመግባት ምእመኑን እስከ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያኑ የመረከብ ስልት ነው፡፡ ይህንም ኬንያ ውስጥ የሚታተመው “The Horn of Africa, Challe nge and opportunity” የተባለው መጽሔት “ዓላማው አዲስ ቤተ ክርስቲያን መመሥረት አይደለም፤ ቤተ ክርስቲያኗን (ኦርቶዶክስን) መለወጥ (ፕሮቴስታንት ማድረግ) እንጂ – The objective is not to set up a new church as such but to introduce reforms within the church” በማለት ገልጾ ነበር፡፡ (The Horn of Africa, Challenge and opportunity, p. 6)

ስለዚህ አዲሱ ስልት “የጥንቷ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ትክክል ነበረች – The ancient orthodox was the right Church” የሚል ነው፡፡ ይህም ማለት ቤተ ክርስቲያንን ከውጭ ከመቃወም ይልቅ ውስጥ ገብቶ ምእመን፣ ካህን፣ መነኩሴ፣ ሰባኪ … መስሎ ከፕሮቴ ስታንት እምነትና ባህል ውጭ ያለውን ነገር ሁሉ “ይህ የጥንቷ ቤተ ክርስቲያን ትምህርት አይደለም፣ ይህን እገሌ የጨመረው ወይም የቀነሰው ነው … ’ እያሉ ቤተ ክርስቲያኗ ኦርቶዶክሳዊ ዶግማዋ፣ ቀኖናዋና ትውፊቷ በሙሉ ጠፍቶ ሙሉ በሙሉ ፕሮቴስታንት እስክትሆን ድረስ መሥራት ነው፡፡

ይህን ስልታቸውንም በኅትመቶቻቸው በይፋ ገልጸዋል፡፡ ለምሳሌም በአንድ ስልታቸውን ይፋ ባደረጉበት መጽሔታቸው ላይ እንዲህ ብለዋል፡-

“ታዲያ እርሷን (የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን) የማዳኑ ሥራ ከየት ይጀምር? እዳር ሆኖ አንዳንድ ምርኮኛን ማፍለሱ የሚፈለገውን የኦተቤን ተሐድሶ ሊያመጣ ይችላልን? አገልግሎቱ ከየት ወደ የት ቢሄድ ይሻላል? ማለት ከውስጥ ወደ ውጭ ወይስ ከውጭ ወደ ውስጥ? በውስጧ እያሉ የወንጌል እውነት ለተገለጠላቸው አገልጋዮቿ እንደ ውጊያ ቀጠና እግዚአብሔር የሰጣቸውን ምሽግ በአሁኑ ጊዜ የማስለቀቅና የጠላትን ወረዳ ከጥቃት ነጻ የማድረግ ሥራ እየተሠራ ያለው በሁለት ወገን ነው፤ … ” ይልና ቀጥሎም ወደ ግባቸው ለመድረስ መደረግ አለበት ያሉትን እንዲህ ዘርዝረዋል፡-

ውስጥ ያሉት እግዚአብሔር በሰጣቸው የውጊያ ቀጣና ውስጥ ሆነው በታማኝነት በእግዚአብሔር ቃል ምስክርነትና በጸሎት ውጊያውን መቀጠል አለባቸው፡፡ በውስጥ ላለው ለዚሁ ውጊያ በወንጌል የታደሱ ክርስቲያኖች ሁሉ እንደ ሙሴ እጃቸውን ወደ ላይ በማንሣት ታላቁን ርዳታ ማድረግና በደጀንነት መቆም ይገባቸዋል፡፡

እነዚህ በወንጌል ተሐደሶ አግኝተናል የሚሉ ሁሉ በውጭ ሆነው ወደ ውስጥ የሚያደ ርጉትን ውጊያ መቀጠላቸው እንደ ተጠበቀ ሆኖ ለውስጠኛው ውጊያ የሚያገለግል ትጥቅ ያላቸውን ወደ ውስጥ ማስገባትና የውስጠኛውን የውጊያ መስመር ማጠናከር ይጠበቅባቸዋል፡፡


“ … በዚህ የተቀናጀ ስልት መንፈሳዊው ጦርነት ቢቀጥል በውስጥ የተሰለፈው ሠራዊት (በተሐድሶ ስም የሚሠራው የፕሮቴስታንት ክንፍ) እያጠቃ ወደ ውጪ ሲገሰግስ፣በውጭ ያለውም (በግልጽ ፕሮቴስታንት ሆኖ የሚሠራው) ከበባውን አጠናክሮ ወደ ውስጥ ሲገፋ እግዚአብሔር በወሰነው ቀን የውስጡና የውጪው ሠራዊት ሲገናኙ በውስጧ የመሸገው ጠላት መሸነፉን በሚመለከት በአንድነት የድል ዝማሬ ሊያቀርቡ ይችላሉ፡፡”
(ኆኅተ ብርሃን፣ መጋቢት 2002 ዓ.ም)

ይህ ሁሉ የሚያሳየው

ሀ) በቤተ ክርስቲያኒቷ ላይ በይፋ የተቀናጀ ጦርነት ያወጁባት መሆኑን፣

ለ) የጦርነቱ አንዱ ስልት ውስጥ ሆኖ በውስጥ አርበኝነት መሥራትና መዋጋት መሆኑን፣

ሐ) የጦርነቱ ዓላማ ጠላት የተባለችውን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ማፍረስ መሆን ነው፡፡


የተሐድሶው ዘመቻ ዘዴዎች ምንድን ናቸው?

ተሐድሶዎች ያሰቡትን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን እንዳለች ፕሮቴስታንታዊ አድርጎ ለውጦ ለመረከብ ያላቸውን ምኞትና ዓላማ እውን ለማድረግ የተለያዩ ዘዴዎችን ይጠቀማሉ፡፡ ከእነዚህም መካከል ሁለቱ የሚከተሉት ናቸው፡፡

ሀ) የሐሰት ውንጀላዎችን መፍጠርና ማሰራጨት ሌባ ሲሰርቅ የሚያየውን ወይም መስረቁን ያወቀበትን ሰው ይወዳል ብሎ ማሰብ ከባድ ነው፡፡ እንደዚሁም እነዚህ በውጫቸው የቤተ ክርስቲያንን ለምድ የለበሱ፣ በውስጣቸው ግን ኦርቶዶክሳዊ የሆነውን እምነትና ባህል አጥፍቶ የምእራባውያን ባህል ተሸካሚ ለማድረግ የሚሠሩ ክፉ ሠራተኞች (ፊል.3÷2) ዓላማቸውንና ስልታቸውን የሚያውቅባቸውን ማንኛውንም ግለሰብም ሆነ ማኅበር አምርረው ይጠሉታል፣ ይፈሩታልም፡፡፡ በእነ ማርቲን ሉተር በአውሮፓ ተካሒዶ ምእራባውያንን ወደ እምነት አልባነትና ክህደት ማድረሱን ዛሬ በተግባር ያስመሰከረውን ተሐድሶ (ፕሮቴስታንት) በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንም ላይ እውን በማድረግ ይሁዳ ስለ ሠላሳ ብሩ ሲል ጌታውንና አምላኩን ኢየሱስ ክርስቶስን ለመሸጥ ከጸሐፍትና ከፈሪሳውያን ጋር “አሳልፌ እንድሰጣችሁ ምን ትሰጡኛላችሁ?” (ማቴ.!1÷05) ብሎ ጌታውን ለሽያጭ እንዳቀረበ፣ እነዚህም ስንቅና ተስፋ የሚሰጧቸውንና ስልት ነድፈው ከርቀት እያሳዩ የሚያሠሯቸውን የላኪዎቻቸውንና የጌቶቻቸውን ምኞት ለማሳካት እንቅፋት ይሆኑብናል የሚሏቸውን ሁሉ ማሩን አምርረው ወተቱን አጥቁረው በማሳየት ስማቸውን በማጥፋት እንዲጠሉ ለማድረግ ይሞክራሉ፡፡

ከዚህ ተግባራቸው ለምሳሌ ያህል ብንጠቅስ በቅዱስ ሲኖዶስ ጸድቆ በተሰጠው ሕገ ደምብ መሠረት በአባቶች ቡራኬና ፈቃድ የተመሠረተውንና በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሥር ሆኖ ዓቅሙ በፈቀደ መጠን ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ዘርፈ ብዙ አገልግሎት በመስጠት ላይ የሚገኘውንና ይህን ለቤተ ክርስቲያናችን እጅግ አደገኛ የሆነ የተሐድሶ እንቅስቃሴ ምንነት በማጋለጥ ለሕዝብ የሚያስረዳውን ማኅበረ ቅዱሳንን ስሙን በኅትመቶቻቸውና በልዩ ልዩ መንገድ ማጥፋትና ሰይጣናዊ አስመስሎ መሳል አንዱ ስልታቸው ነው፡፡ ለአብነት ያህልም የሚከ ተሉትን እንመልከት፡-


“ማቅ (ማኅበረ ቅዱሳን) ያለ እኔ ቤተ ክርስቲያን፣ ሀገርና መንግሥት የለም ብሎ በጭፍን የሚያስብ ስለሆነ በቤተ ክርስቲያኒቱ ሌላ መንፈሳዊ ማኅበርም ሆነ ጉባኤ ለማየት ዓይኑ የተሸፈነ ነው፡፡ ራሱን የቅዳሴ፣ የቅኔና የመጻሕፍት ማስመስከሪያ ቤተ መምህራን አድርጎ በማየቱ በእርሱ እጅ ፈቃድ ያላገኙ ሰባክያንና መዘምራን ቢፈጠሩ የተለመደው የኮሚኒስቶች ፍልስፍና (የሀሰት ስም የማጥፋት ቅስቀሳውን) ያወርድባቸዋል፡፡”
(መጥቅእ፣ ኅዳር 2002፣ ገጽ 1፣ርእሰ አንቀጽ)

እንግዲህ ይህን የሚለው አካል በግልጥ ቤተ ክርስቲያኒቱ ተሐድሶ ያስፈልጋታል እያለ በዚሁ ጋዜጣ የገለጸው የተሐድሶ ድርጅት ነው፡፡ ልዩነቱ የዓላማ መሆኑን ራሳቸው ተናግረው ሲያበቁ እንደገና መልሰው ተሐድሶ መባልን የሐሰት ስም ማጥፋት ዘመቻ ነው ይላሉ፡፡ አንባቢዎቻቸው ይህን እንኳን ማገናዘብ አይችሉም ብለው ይሆን?

“የማኅበረ ቅዱሳን ትምህርት እግዚአብሔር ፍጹም ጨካኝ ስለሆነ ስለማይሰማንና በርኅራሄ ከእርሱ የተሻሉ ቅዱሳን በፊቱ ቆመው እንዲለምኑልን የእነርሱ ልመና ግድ ብሎት ስለሚምረን በአማላጅነት እንመን ይላል፡፡” (ይነጋል፣ 1997 ዓ.ም. ገጽ 123) “ማኅበረ ቅዱሳን የተባለው ይህ የሰይጣን ማኅበር አሁን ወደ ነፍሰ ገዳይነት ሊገባ ራሱን እያዘጋጀ ነው፡፡” (ይነጋል፣ 1997 ዓ.ም.ገጽ 127) ይህ የስም ማጥፋት ዘመቻ በሀገር ውስጥ ባሉ ሚዲያዎች ብቻ የተወሰነ ሳይሆን ዋናው የተሐድሶ ዘመቻ አርቃቂዎችና ስልት ነዳፊዎች በሆኑት በምእራባውያን ፓስተሮችም በብዛትና በዓይነት የሚሠራ ሥራ ነው፡፡ ለምሳሌ ያህልም ዊሊያም ብላክ የተባለው አሜሪካዊ ፓስተር አናሲሞስ በተባለው የጦማር መድረኩ ላይ የኢትዮጵያን ቤተ ክርስቲያን እንዴት ማፈራረስ እንደሚቻልና በአሁኑ ወቅትም የእርሱና መሰል ድርጅቶች ቤተ ክርስቲያንን እንዴት እየተዋጓት እንደሆነ “Struggle for the soul of the Ethiopian orthodox Church” በተሰኘው ጽሑፉ ላይ በሰፊው ገልጧል፡፡ የፕሮቴስታንት ጉዳይ አስፈጻሚ የሆነው የተሐድሶ አንቅስቃሴ ምን ማለት መሆኑን ለዓላማቸው መሳካት እንቅፋት ሆኖብናል ያለውን ነገር ሲናገር ገልጾታል፤ እንዲህ ሲል፡-

“Working against both the ongoing creep of Western values and the attempts by Reformists to restore the church, a reactionary movement called Mahebere Kidusan and led by members of the hierarchy and priests and others, are seeking to fend off any changes and to preserve aspects of the Church which they feel are crucial to their identity and Ethiopia’s place in the world. …

በሀገሪቱ ውስጥ እየተንሰራፋና ሥር እየሰደደ ያለውን ምእራባዊ ባህልና በተሐድሶ አራማጆች ቤተ ክርስቲያኒቷን ለማደስ የሚደረገውን ጥረት ሁለቱንም የሚቃወምና ለዚህም እየሠራ ያለ አድኃሪ የሆነ ማኅበረ ቅዱሳን የሚባል እንቅስቃሴ አለ፡፡ ይህ ማኅበርም ቤተ ክርስቲያንን ለመለወጥ የሚደረገውን ማንኛውንም ነገር ለመከላከልና ለራሳቸው ማንነትና ኢትዮጵያ በዓለም ስላላት ቦታ አስፈላጊ ነው የሚሉትን የቤተ ክርስቲያኒቷን ገጽታ ለመጠበቅ ይፈልጋሉ፡፡”

http://www.Compassdirect.org/english/country.ethiopia/11092/ተሐድሶዎች ቤተክርስቲያናቸውን የሚወዱትንና ለእምነታቸውና ለሥርዓታቸው ተቆርቋሪ የሆኑትን ምእመናን፣ ካህናት፣ መነኮሳት … ሁሉ ማኅበረ ቅዱሳን የሚባል ነገር መኖሩን ከነ ጭራሹ ያልሰሙ ሰዎች ቢሆኑም እንኳ “ማኅበረ ቅዱሳን (ማቅ)” ናቸው የሚል ታርጋ በመለጠፍ ለማሸማቀቅ ይሞክራሉ፡፡ በዚህም የተሐድሶ ጉዳይ የሌለና የሆኑ ቡድኖች ጠብና ሽኩቻ ብቻ ተደርጎ እንዲታይ ይጥራሉ፡፡ እጅግ በጣም ብዙ የሆኑ ለማመን የሚከብዱ የበሬ ወለደ ዓይነት የስም ማጥፋት ወሬዎችን በማኅበሩ ላይ በማሰራጨት ላይ ናቸው፡፡ ለምሳሌም በቅርቡ “የማኅበረ ቅዱሳን የሃያ አምስት ዓመት ስትራቴጂ ነው” በሚል ስም አንድን ሕፃን እንኳ ሊያሳምን በማይችል መልኩ ራሳቸው የፈጠሩትን አሉባልታ የማኅበሩ አስመስለው በሐሰት ማኅተም አትመው በኢንተርኔት አሰራጭተዋል፡፡ እንዲህ ዓይነት የፈጠራ ክሶችንና ስም ማጥፋቶችን ደህና አድርገው ተያይዘዋቸዋል፡፡

ለ) የቤተ ክርስቲያኒቱን አስተዳደርና መዋቅር መቆጣጠር ተሐድሶዎች ቤተ ክርስቲያኒቷን ለመለወጥና ለዓላማቸው ማስፈጸሚያ የተመቸች ለማድረግ ይረዳቸው ዘንድ ለመቆጣጠር የሚመኙት አንዱ ነገር የቤተ ክርስቲያኒቱን አስተዳደርና መዋቅር መያዝ ነው፡፡ ይህን ማድረግ ከቻሉ በቤተ ክርስቲያኒቱ አንደበት በመናገር፣ ቤተክርስቲያን ያልሆነችውን ናት፣ የሆነችውን ደግሞ አይደለችም በማለት ያሰቡትን የተሐድሶ ዓላማ ከግብ ለማድረስ ይረዳቸዋል፡፡

ወደዚህ ግብ ለመድረስም በተለያዩ ጊዜያትና ስልቶች ከመሪጌቶች፣ከቀሳውስት፣ ከመነኮሳት፣ ከዲያቆናትና ከሌሎችም መካከል በተለያየ ጥቅማ ጥቅምና ድለላ የማረኳቸውንና ያሰለጠኗቸውን ሰዎች በአስተዳደር መዋቅሩ ውስጥ ለማስገባትና ቦታውን ለመያዝ ደፋ ቀና በማለት ላይ ናቸው፡፡ በዚህም የተወሰነ ርቀት መጓዝ ችለዋል፡፡ ይህም በስልታቸው እንደ ገለጹት “መንፈሳዊ ቀውስ የደረሰበትን አስተዳደር ማረምና ማስተካከል” (ኆኅተ ብርሃን፣ መጋቢት2000፣ ገጽ 16) በሚል ሽፋን የሚካሔድ ነው፡፡

ይህን ጉዳይ እስከ የት ድረስ መግፋትና ማድረስ እንደሚፈልጉ ሲገልጹም እንዲህ ብለዋል፡-

“ማቅ (ማኅበረ ቅዱሳን) ወደደም ጠላም ቤተ ክርስቲያኒቱ በእውነት በሚወዷትና የወንጌልን እውነት በሚያገለግሉ መምህራንና ሊቃውንት ይህንም እውነት ተቀብለው አምላካቸውን በንጹሕ ልብ ሆነው በሚያመልኩ፣ በተለይም መጪው ዘመን በትካሻቸው ላይ የወደቀባቸው ከመንፈሳዊ ኮሌጆቻችን እየተመረቁ የሚወጡ የወንጌል አርበኞችና ቤተ ክርስቲያንን ይጠብቁ ዘንድ እግዚአብሔር ጳጳሳት አድርጎ የሾማቸው አባቶች በሚወስዱት የማያዳግም እርምጃ ቤተ ክርስቲያናችን ተሐድሶን ታደርጋለች፡፡” (መጥቅእ፣ ኅዳር 2000፣ ገጽ 2) ጳጳሳት ሳይቀሩ የማያዳግም እርምጃ መውሰዳቸውና ቤተ ክርስቲያኒቱን ማደሳቸው የማይቀር መሆኑን በግልጽ ተናግረዋል፡፡ ስለሆነም ይህን ሕልማቸውን እውን ለማድረግ የቤተ ክርስቲያኗን የአስተዳደር መዋቅር፣ እስከ ጵጵስና ደረጃ ያለውንም መቆጣጠር ዋና ስልታቸው ነው፡፡

ዛሬ የመነኮሱበት የማይታወቅ ሰዎች የአባቶቻችንን ቆብ አጥልቀው መስቀሉን ጨብጠው ቀሚሱን አጥልቀው ካባውን ደርበው፣ ያልሆኑትን መስለው፣ ሌሎችም የነበሩ፣ ዛሬ ግን ያልሆኑ፣ ዓላማቸውን እንደ ይሁዳ ለውጠው የክፋቱ ተባባሪ ሆነው ያሉ ሁሉ በቤተ ክርስቲያኗ ስም ሲጫወቱ ዝም እየተባሉ ስለሆነ እነዚህ ሰዎች የነገዪቱ ጳጳሳት የማይሆኑበት እድል አይኖርም ብሎ ማሰብ አይቻልም፡፡

ይልቁንም አሁን ሃይማኖታቸው በግልጽ ፕሮቴስታንት (ተሐድሶ) የሆኑና ብዙ ጉድ ያለባቸው፣ የምግባር ድቀት ያንገላታቸው፣ የሃይማኖት አባት ሆነው ምእመናንን ለማስተ ማርና ለመምራት ቀርቶ ተነሳሒ ለመሆን እንኳ የከበዳቸው ሰዎች ዓይናቸውን በጨው ታጥበው ጵጵስና ለመሾም የሲኖዶስ ስብሰባ በመጣ ቁጥር አፋፍ ላይ እየደረሱ እየተ መለሱ ነው፡፡ ይህ ሁኔታ እንዲሁ ከቀጠለ እነዚህ ሰዎች አንድ ቀን የጳጳሳትን አስኬማ ደፍተው፣ በትረ ሙሴ ጨብጠው፣ “አቡነ” እገሌ ተብለው ላለመምጣታቸው ምን ዋስትና አለ? “ሞኝ ቢቃጡት የመቱት አይመስለውም” እንደሚባለው እንደ እነዚህ ዓይነት ሰዎችን ለጵጵስና እጩ አድርጎ እስከማቅረብ ደረጃስ እንዴት ሊደረስ ቻለ?

ማንነታቸው ተጣርቶ በንስሐ የሚመለሱት ቀኖና ሊሰጣቸው፣ የማይመለሱት ደግሞ ሊለዩ (ሊወገዙ) ሲገባቸው የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ሆነው በቤተ ክርስቲኒያቱ ህልውና ላይ ወሳኝ አካላት ሊሆኑ መታሰቡ በራሱ የሚያሳየው ከባድ ነገር አለ፡፡

እነዚህን ሰዎች በአድባራትና በገዳማት ዕልቅናና በተለያየ ሓላፊነት ከመሾም ጀምሮ ግልጽ የሆነ የአደባባይ ጉዳቸውን ዝም ከማለትና አልፎ አልፎም ከማበረታታት ጀምሮ በቤተ ክርስቲኒያቱ አስተዳደር ውስጥ እንዳሻቸው እንዲናኙበት የሚፈቅድና የሚመች የተሐድሶ ሰንሰለት አለማለት ይሆን?

እውነተኛ የቤተ ክርስቲያን ልጆችና አባቶች እንደ እንጀራ ልጆች እየተቆጠሩና እየተገፉ እነዚህ ተሐድሶዎች ደግሞ ባለሟሎች መስለው ከዚያም አልፎ ለጵጵስና ታጭተው ማየትና መስማት በእጅጉ ያማል፣ ልብንም ያደማል፡፡ ስለዚህ እነዚህ ሰዎች አናት ላይ ወጥተው የጵጵስና መዓርግ ጨብጠው ከመጡ በኋላ በቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ ሊያመጡ ያሰቡትን ስልታዊ አደጋ መገመት ውኃን የመጠጣት ያህል ቀላል ነው፡፡

ስለሆነም እነርሱ ያሰቡት ከባድ ትርምስ ሳይመጣ ‹ሳይቃጠል በቅጠል› እንዲሉ በጊዜ ከጸሎት ጀምሮ ማንኛውም ሊደረግ የሚገባውን የመከላከል ሥራ ከወዲሁ መፈጸም ይገባል፡፡ ቁጭ ብሎ የሰቀሉትን ቆሞ ማውረድ ያቅታልና፡፡ ይህም “እነ እገሌ ምን እየሠሩ ነው?” በሚለው ያልጠቀመን ፈሊጥ ሳይሆን “እኔ ምን አደረግሁ?

አሁንስ ምን ማድረግ አለብኝ?” በሚል ሊሆን ይገባል፡፡ የቤተ ክርስቲያን አምላክ እግዚአብሔር በቤቱ የተሰገሰጉ ይሁዳዎችን የሚያጋልጥበትንና ከመንጋው የሚለይበትን ዘመን ያቅርብልን፣ አሜን፡፡

መልአከ ገነት ኃይለ ማርያም ፋንታሁን

መልአከ ገነት ኃይለ ማርያም ፋንታሁን አረፉ።

ከባህር ዳር ማእከል

ሰኔ 9 ቀን 2003 ዓ.ም

መልአከ ገነት ኃይለ ማርያም ፋንታሁንበባህር ዳር ከተማ በሚገኘው ፈለገ ገነት ቅዱስ ጊዮርጊስ ገዳምን ከ40 ዓመት በላይ በአስተዳዳሪነት ያገለገሉት መልአከ ገነት ኃይለ ማርያም ፋንታሁን በጠና ከታመሙ በኋላ በተወለዱ በ80 ዓመታቸው ግንቦት 30 ቀን 2003 ዓ.ም ከምሽቱ 2፡00 ሰዓት አርፈዋል። 

ሥርዓተ ቀብራቸው ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ፣ ብፁዕ አቡነ ኤልያስና ብፁዕ አቡነ ቶማስ፣ ብፁዕ አቡነ ማርቆስ እንዲሁም ወዳጅ ዘመድና ቤተሰቦቻቸው በተገኙበት በፈለገ ገነት ቅዱስ ጊዮርጊስ ገዳም በዕለተ ሐሙስ ሰኔ 2 ቀን 2003 ዓ.ም ከቀኑ 5፡30 ተፈጽሟል፡፡

 
መልአከ ገነት ኃይለ ማርያም ከአባታቸው መምህር ፋንታሁን ጥሩነህ እና ከእናታቸው ወ/ሮ ውዴ አካሌ በምዕራብ ጎጃም ዞን በሜጫ ወረዳ በደብር መድኃኒት ማርያም ልዩ ስሟ ደረመኔ በተባለ ቦታ የተወለዱ ሲሆን እድሜያቸው ለትምህርት እንደደረሰ አባታቸው ተተኪ አገልጋዮችን ለማፍራት ባላቸው ልዩ ፍላጎት የተነሣ መንፈሣዊ ትምህርት ቤት በመግባት የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት በትጋት በመማር እንዲሁ ደግሞ ወንበር ዘርግተው በማስተማር፣ ተተኪ ካህናትንና መምህራንን በማፍራት፣ ለከፍተኛ ማዕረግ የበቁ ጳጳሳትን በማፍራት፣ ከ300 በላይ መነኮሳትን አመንኩሰዋል። ከመነኮሱት ውስጥም ለፓትርያርክነት ማዕረግ የበቁ ያሉበት ሲሆን ፈለገ ገነት ቅዱስ ጊዮርጊስ ገዳምን ለ43 ዓመታት በማስተዳደር፣ በቤተ ክርስቲያኒቷ የተለያዩ የልማት ሥራዎች ላይ በመሣተፍ፣ ችግረኞችን በመርዳት፣ የተጣሉትን በማስታረቅ፣ ያዘኑትን በአባታዊ ምክር የሚያረጋጉ አባት እንደነበሩ አጭር የሕይወት ታሪካቸው ያስረዳል።  
አሻራ አዲስ መንፈሳዊ ተውኔት

አዲስ መንፈሳዊ ተውኔት ይመረቃል

በይበልጣል ሙላት

ሰኔ 6፣2003ዓ.ም

በማኅበረ ቅዱሳን የአዲስ አበባ ማዕከል የትምህርትና ኪነጥበባት ክፍል የተዘጋጀውና “አሻራ” የሚል ስያሜ የያዘው ተውኔት ይመረቃል፡፡

ተውኔቱ እሑድ ሰኔ 12 ቀን 2003 ዓ.ም ከቀኑ 8፡00 በማኅበረ ቅዱሳን ህንፃ እንደሚመረቅ የተገለጸ ሲሆን ከዚያ በኋላ ለምዕመናን ክፍት ይሆናል ተብሏል፡፡

  አሻራ አዲስ መንፈሳዊ ተውኔት
የተውኔቱ አስተባባሪ አቶ አበራ ምታው ስብከተ ወንጌል በተለያየ ዘዴና መልክ እንደሚተላለፍ ገልጸው የሰዎችን ቀልብ ስቦ በመያዘ በቀላሉና በማይረሳ መልኩ ለማስተማርና ሃይማኖታዊ መነቃቃትንም ለመፍጠር እንደሚጠቅም አስገንዝበዋል፡፡

ተውኔቱ ሕዝበ ክርስቲያኑ ቅርሱን እንዴት? ከማን? እና መቼ? መጠበቅ እንዳለበት እንዲሁም እስከምን ድረስ መስዋዕትነት መክፈል እንዳለበት የሚያስገነዝብ ሲሆን ስለ ሃይማኖት ጽናትና ስለመንፈሳዊ ጥበብም እንደሚያስተምር አያይዘው ዓላማውን ገልጸዋል፡፡

በተውኔቱ 12 ሰዎች የተሳተፉ ሲሆን ለማዘጋጀትም ከአንድ ዓመት ጊዜ በላይ ፈጅቷል፡፡ በዝግጅት ወቅት የተለያዩ ችግሮችን እንዳለፉ የገለጹት አቶ አበራ በተለይ የመለማመጃ ቦታ አለመመቸት፣ የበጀት በጊዜው አለመድረስና የተዋንያኑ የሥራ መደራረብ ችግር እንደፈጠረባቸው አልሸሸጉም፡፡

ይህ ተውኔት ሕዝበ ክርስቲያኑ በዚህ መንገድ ስብከተ ወንጌልን ማስፋፋት እንደሚቻል ለማስገንዘብ የበኩሉን ድርሻ እንደሚወጣና ደራስያን ተዋንያንና ሌሎች የኪነጥበብ ባለሙያዎች ከዚህ ዘርፍ በመሳተፍ ክርስቲያናዊ ግዴታቸውን እንዲወጡ ያበረታታል ሲሉ አቶ አበራ ያሳስባሉ፡፡

በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ አባቶችና ጥሪ የተደረገላቸው ምዕመናን እንደሚገኙ ይጠበቃል፡፡

 

Debub_Omo1.jpg

በኦሞ ወንዞች ዙሪያ ተስፋ የሚያደርጉ ዓይኖች!

በማኅደረ ታሪኩና ተ/ሥላሴ ጸጋ ኪሮስ
ሰኔ 03፣ 2003 ዓ.ም 
 

Debub_Omo1.jpg

 
ከሐመር ብሔረሰብ አባላት ለአንዱ፣ የፈጠራችሁ ማን ነው? ብላችሁ ጥያቄ ብታቀርቡ በእምነት በጠጠረ፣ ጥያቄያዊ በሆነ ፊትና የዋሕ ልቡና “ቦርጆ ነዋ! ቦርጆ፣ ከእርሱ በረከት ያልተቋደሰ፣ በእርሱ እቅፍ ውስጥ የሌለ፣ እርሱ ያላበላው፣ እርሱ ያላጠጣው ማን አለ? እርሱ ሁሉን በፍቅር የሚንከባከብ፣ ሕፃናትን የሚያሳድግ የፍቅር አምላክ ነው” ይሏችኋል፡፡

በዚህም አያቆሙም “ቦርጆ በእኛ መካከል ሲኖር ነበር፣ በቆይታ አንዳንዶችDebub_Omo22.jpg በልባቸው ክፉ አስበው አስቀየሙት፣ ቦርጆን ገረፉት፣ መቱት፣ አቆሰሉት፡፡ እርሱም ከእንግዲህ ‘ከእናንተ ጋር ሆኜ /እየኖርኩ/ የማበላችሁ የማጠጣችሁ አይምሰላችሁ፡፡ ወደ ሰማይ እሄዳለሁ በልባችሁ ግን ለምኑኝ አበላችኋለሁ፣ አጠጣችኋለሁ’ ብሎን ሄዷል፡፡” በማለት ስለ አምላካቸው ያብራራሉ፡፡

 
ብዙ ጥናት የሚጠይቅ ጉዳይ ቢሆንም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ይገልጻል፡፡ የደቡብ ኢትዮጵያን ክፍል አቡነ ተክለሃይማኖት፣ አቡነ ዜና ማርቆስ እና ሌሎችም ቅዱሳን አበው የደከሙበት፣ የወንጌልን የምሥራች፤ የጌታችንን በዚህ ዓለም ከእኛ ጋር ተመላልሶ ማስተማሩን፣ አበርክቶ ማብላቱን፣ ተአምራት ማድረጉን፣ መገረፉን፣ መሰቃየቱን፣ መሰቀሉን፣ መሞቱን፣ መነሣቱን፣ ማረጉን ያስተማሩበት፣ ያመኑትንም ያጠመቁበት፣ በኪደተ እግራቸው የባረኩት ምድር ነው፡፡ ማን ያውቃል ይሄ የቦርጆ ትርክት ከዚያ መጥቶ ቢሆንስ? ለአሁኑ እግረ መንገዳችንን አንሣነው እንጂ ጉዳያችን ይሄ ሆኖ አይደለም፡፡ በደቡብ ኦሞ ሀገረ ስብከት እየተሠራ ያለውን ስብከተ ወንጌል የማስፋፋት አቢይ ተግባርና ተያያዥ ጉዳዮችን በአጭሩ ለመቃኘት እንጂ፡፡
 
ሀገረ ስብከቱ
ከአዲስ አበባ 781 ኪ.ሜ. ርቀት ላይ መቀመጫውን ጂንካ ከተማ ያደረገው የደቡብ ኦሞ ሀገረ ስብከት በሥሩ ዘጠኝ ወረዳዎች ያሉት ሲሆን በእነዚህ ወረዳዎች እስከ 1998 ዓ.ም 29 አብያተ ክርስቲያናት ታንጸው ነበር፡፡
በዞኑ 440.623 የሚጠጋ ሕዝብ ያለ ሲሆን ከእነዚህም 24.35 በመቶው የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታዮች ቀሪዎችም የባዕድ አምልኮ የተወሰኑትም የሌሎች እምነት ተከታዮች ናቸው፡፡
ከ16 ያላነሱ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ይገኛሉ፡፡ ከእነዚህም ሐመር፤ በና፤ ፀማይ፤ ካሮ፤ ዲሚ፤ ባጫ፣ ዳሰነች፣ ኤርቦሬ፣ ማሊ፣ አሪ፣ በዲ፣ ሙርሲና የመሳሰሉት ይገኙበታል፡፡

ዋላ ወደ ውሃ ምንጭ እንደሚናፍቅ ነፈሴ ወደ ሕያው አምላክ ተጠማች፡፡

በሀገረ ስብከቱ የሚገኙት አብያተ ክርስቲያናት የታነፁት ከተማን መሠረትDebub_Omo15.jpg አድርገው በመሆኑ ከ90 በመቶ በላይ የሚሆነውን የገጠራማ ቀበሌዎች ሕዝብ ያገናዘበ አልነበረም፡፡ ስለዚህም የገጠሩ ሕዝብ መጠመቅ እያማረው ሳይጠመቅ፣ መማር እያማረው ሳይማር፣ መስቀሉን መሳለም እያማረው ሳይሳለም፤ ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ “ዋላ ወደ ውሃ ምንጭ እንደሚናፍቅ ነፍሴ ወደ ሕያው አምላክ ተጠማች” እንዳለው ነፍሳቸው አምላክን እንደናፈቀችና እንደተጠማች ብዙ ቀኖች መሽተው ብዙ ሌሊቶች ነግተዋል፡፡ መዝ 41፥1

አንድ የአካባቢው ምእመን ‹‹ከእንግዲህ ብሞትም አይቆጨኝ፤ ሥጋዬ እንዲሁ በየሜዳው አይወድቅምና ይህ የዕድሜ ዘመኔ ሙሉ ናፍቆቴ ነበር” የሚለው ንግግራቸው የናፍቆታቸውን ልክ ያሳያል፡፡

Debub_Omo13.jpgየሀገረ ስብከቱ ሊቀጳጳስ ብፁዕ አቡነ ዕንባቆም በየቦታው በሚደርሱበት ጊዜ የሚኖረው አቀባበልና የሕዝቡ ስሜት፥ ለመጠመቅ ያለው ጉጉት ልዩ ነበር፡፡ አባታችን “ዝናብ አምጡልን የሚለው” የሽማግሌዎች ጥያቄ በፈጣሪ ያላቸውን ተአምኖ ያሳያል፡፡ አንድ አረጋዊ አባትም “እኛ እድላችን ሆኖ ታቦት በመምጣቱ እናመሰግናለን፡፡ አባታችንም በመምጣታቸው ደስ ብሎናል” በማለት በአስተርጓሚ ሲናገሩ በልዩ ስሜት ነበር፡፡

በቅርብ ጊዜ ሀገረ ስብከቱ ለሚያደርገው አብያተ ክርስቲያናትን የማነጽ፣ የመሠረት መስቀል የማስቀመጥ ሰፊ እንቅስቃሴ፥ ማኅበረሰቡ ሁሉ ርስቱ፣ ጉልቱ ማንነቱ የሆነውን መሬቱን በገዛ ፈቃዱ ነበር ቆርሶ የሰጠው፡፡ ይሄም የማኅበረሰቡን ለዚህች ቤተ ክርስቲያን ያለውን ፍቅርና ጉጉት አጉልቶ የሚያሳይ ታሪካዊ ክንዋኔ ነው፡፡

ከዚህም በላይ አንደኛው ሲጠመቅ ሌላኛው እኛስ መቼ ነው የምንጠመቀው? እያሉ ሀብተወልድና ስመ ክርስትና የሚያገኙበትን ቀን በመናፈቅ የሚያቀርቡት ጥያቄ ብፁዕነታቸው በደረሱበት ካህናትም በታዩበት ሁሉ የሚያጋጥም ነው፡፡

የቅዱስ ሲኖዶስ ትኩረትና የሀገረ ስብከቱ ምላሽ

እነዚህ ሕዝቦች ምንም እንኳን ክርስትናን ቢናፍቁም የተለያዩ ምክንያቶች ፍላጎታቸው እንዳይማላ እንቅፋት ተደርገው ሊጠቀሱ ይችላሉ፡፡ ሀገረ ስብከቱ በሰሜን ኦሞ ሀገረ ስብከት በሞግዚትነት መተዳደሩ አንደኛው ሲሆን ብሔረሰቦቹ ወደ ሰፈሩባቸው ቦታዎች ለመጓዝ በእግርና በበቅሎ እንጂ በተሽከርካሪ አስቸጋሪ መሆናቸው ይሄንንም ተቋቁሞ ለማስተማርና ለመቀደስ የሚችሉ በቂ ካህናት አለመኖራቸው እንደዋነኛ ምክንያት ይወሰዳሉ፡፡

ይሁንና ቅዱስ ሲኖዶስ ለቦታው በሰጠው ትኩረት ከ1998 ዓ.ም ወዲህ ሀገረ ስብከቱ ራሱን ችሎ መንበሩን ጅንካ ከተማ ላይ ተክሎ እንዲንቀሳቀስ ፈቅዶ ሊቀ ጳጳስ መድቦለታል፡፡

ሀገረ ስብከቱ ለውጦችን ለማምጣት እያደረገ ያለው እንቀስቃሴ የሚበረታታ እንደሆነ የተሠሩት ሥራዎች ያሳያሉ፡፡

Debub_Omo9.jpg90 በመቶ የሚሆነውን የሕብረተሰብ ክፍል ያማከሉ በተጨማሪ 37 ቦታዎች ላይ የመሠረት መስቀል ተቀምጧል፡፡ ወደፊት ቤተ ክርስቲያን እንደሚሠራባቸው ተስፋ ይደረጋል፡፡ ለጊዜው የአካባቢው ምእመናን በየዋሕ ልቡናና በፍጹም እምነት ቦታዎችን እየተሳለመ ይጠብቃቸዋል፡፡

እንደ ደራሽ ውሃ ድንገት አጥምቁን እያሉ በርካቶች እስከ አሁን እየመጡ ይገኛሉ፡፡ በዞኑ ከሚገኘት የተለያዩ የሕብረተሰብ ክፍሎች 50,000 የሚሆኑትን በማጥመቅ የሥላሴ ልጅነትን እንዲያገኙ የተደረገው ጥረት እጅግ የሚያበረታታ ነበር፡፡

ተባርከው የመስቀል ምልክት ከተደረገባቸው 37ቱ ቦታዎች የ16ቱ ግንባታDebub_Omo24.jpg ተጀምሯል፡፡ ከእነዚህም 6ቱ ለአገልግሎት ዝግጁ ሆነው በ3ቱ አገልግሎት መሥጠት ተጀምሯል፡፡  አማኞችን ለማብዛት፣ ያመኑትን ለማጽናት፣ ቀድሶ ለማቁረብ በቋንቋቸው የሚያስተምራቸው የአካባቢው ተወላጅ ያስፈልጋቸዋል፡፡ ከተጠመቁትም ካልተጠመቁትም የሕብረተሰብ ክፍሎች መካከል የአብነት ትምህርት እንዲማሩላቸው ፈቃደኛ የሆኑትን ልጆቻቸውን ሙሉ ወጪአቸውን በመሸፈን ጂንካ ከተማ በሚገኘው የአንቀጸ ብፁዓን አቡነ ተክለሃይማኖት ገዳም ገብተው እንዲማሩና የዲቁና ማዕረግ እንዲያገኙ ማድረግ ተችሏል፡፡ በዚህም ከወዲሁ አገልጋዮችን ለማግኘት የማስቻል ሥራን ያጠናክራል፡፡ ከዚህ ሁሉ የብፁዕ አቡነ ዕንባቆም ትጋትና ኖላዊ አባግዐነት ዋናውን ስፍራ የሚይዝ ነው፡፡

Debub_Omo27.jpgብፁዕነታቸው ከየብስ እስከ የባሕር ላይ ጉዞ፣ ከጂንካ እስከ ኬንያ ጠረፍ፣ ከእግር ጉዞ በሞተር ላይ ተፈናጥጦ እስከ መጓዝ ድረስ በ16ቱም የብሔረሰብ አባላት ዘንድ እየተገኙ ከደከመኝ ሰለቸኝ፣ ሕመም ተሰምቶኛልና ዛሬን ልረፍ፣ ዛሬ አይመቸኝም አልገኝም፣ ዙፋን ዘርጉልኝ ምንጣፍም አንጥፉልኝ ሳይሉ፣ እንደቀየው አብረው ተመግበው፣ ከሃገር ሽማግሌዎች ጋር በአንድ እቃ ቦርዴ ፉት በማለት ጠጥተው ማኅበረሰቡን መስለውና ተዋሕደው አፅናንተዋል፣ መክረዋል፣ አስተምረዋል፣ አጥምቀዋል፡፡ የሕፅናትን መዝሙር፣ የወጣቶችን ጭፈራ፣ የሽማግሌዎችን ምርቃት ተቀብለዋል፡፡
 
ቀሪ ተግባሮች

ይህ ሁሉ ሆኖ አሁንም ብፁዕነታቸውን የሚያሳስባቸው የአብያተ ክርስቲያናት መታነጽ፣ የማኅበረሰቡ በአንዲት ተዋሕዶ ጥላ ሥር መሰብሰብ ነው፡፡ “ከአሥራ ስድስቱም ወረዳዎች በርካታ ወገኖችን አጥምቀናል እያጠመቅንም ነው፡፡ በዝግጅት ላይ ያሉ እነዚህ ወገኖች ቤተ ክርስትያን ያስፈልጋቸዋል፣ ለወገን ደራሽ ወገን ስለሆነ በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ ያለን ለእነዚህ ወገኖች እንድረስላቸው፤ በሚያልፈውም ገንዘብ የማያልፈውን ርስት መንግሥተ ሰማያትን እንድንወርስ ጥሪዬን አስተላልፋለሁ” በማለት ያሳስባሉ፡፡

ቀደም ተብሎ እንደተገለጸው በርካታ ሥራዎች ቢሠሩም ገና የቀሩ ሥራዎች እንዳሉ መረዳት አያዳገትም፡፡ የሰው ሕንፃ መሠረት ተጣለ እንጅ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን የላቸውም፡፡ የብፁዕነታቸው ንግግርም ይሄንን ይገልጻል፡፡ የመሠረት መስቀል ከተቀመጠባቸው ቦታዎች 88 በመቶው የሚሆኑት አብያተ ክርስቲያናት ያልታነፁባቸው በመሆኑ ሕብረተሰቡ መስቀሎቹን በመሳለም የቀሪዎቹን ወገኖች መጠመቅ፣ የእነርሱን ዕለት ዕለት ሥጋ ወደሙ መቀበል፣ በቅፅረ ቤተ ክርስቲያን ጸሎት ማድረስን ተስፋ እያደረጉ ይገኛሉ፡፡

የሀገረ ስብከቱን አገልግሎት ከባድ አድርጎ የቆየው አንዱ ጉዳይ የሚሰጠው ትምህርተ ወንጌል በአስተርጓሚ መሠጠቱ ነው፡፡ ከየብሔረሱ ሰዎች አዲስ አበባ ድረስ አምጥቶ በማሰልጠን መልሶ ወደ አካባቢያቸው ማኅበረሰብ በመላክ ገብተው በቋንቋቸው እንዲያስተምሩ በማድረግ አጥጋቢ ውጤት ማግኘት ተችሏል፡፡ ይህ ሥራ በዋነኝነት ተጠናክሮ ሊቀጥል ይገባዋል፡፡ ለዚህም በጀት፣ አሠልጣኝ፣ የሥልጠና ቦታና ቁሳቁስ ያስፈልጋል፡፡ ይህም ከየትም አይመጣም፣ ከምእመናን እንጅ፡፡

በተለይም በእነዚህም በረሀማና ጠረፋማ በሆኑ አካሳቢዎች የወንጌል አልግሎት በዘላቂነት የሚዳሰስበትን መንገድ መቀየስ ያስፈልጋል፡፡

የሰማይ አምላክ ያከናውንልናል እኛ ባርያዎቹ ተነስተን እንሠራለን፡፡

የተጠቀሱት ችግሮች አጣዳፊ ምላሾችን የሚፈልጉ እንዲሁም በረጅም ጊዜ እቅድ የሚሠሩ ናቸው፡፡ አብዛኛዎቹም የምእመናንን ርብርብ የሚጠይቁ እንደሆነ ግልጽ ነው፡፡

Debub_Omo10.jpgይህንን ለማስተባበር የሚችል በሀገረ ስብከቱ ሊቀጳጳስ በብፁዕ አቡነ ዕንባቆም የሚመራ አንድ ዐቢይ ኮሚቴ ተቋቁሟል፡፡ “የደቡብ ኦሞ ሀገረ ስብከት ስብከተ ወንጌል ማስፋፊያልማትና ልማትና ሕንፃ ቤተ ክርስትያን አሠሪ ኮሚቴ” በሚል ስያሜ የተቋቋመው ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ ኢ/ር ዳንኤል ኃይለ “እኛ ተነስተናል የሰማዩ አምላክ ያከናውንልናል፡፡ ሕዝቡ ምኞቱ የመሠረት መስቀል የተሠራባቸውን ቦታዎች ቤተ ክርስቲያን ተሠርቶ ማየት ነው፡፡ ስለዚህ የመሠረት መስቀል የተተከለባቸው 37ቱ አብያተ ክርስትያናት እስኪሠሩ ድረስ፣ ስብከተ ወንጌል በአሥራ ስድስቱም ብሐሮች ቋንቋ እስኪሰበክ ድረስ እንተጋለን፡፡” የሚሉት ምክትል ሰብሳቢው ይቀጥሉና “ይህንን ለማድረግ የአጭር፣ የመካከለኛና የረጅም ጊዜ ስልታዊ ዕቅድ በመዘርጋት ከየብሔረሰቦች ዲያቆናትን፣ ካህናትን፣ መምህራንን አምጥቶ በማሰልጠን እናወጣለን ብለን እናስባለን፡፡ ይህንንም ከእግዚአብሔር ጋር እናሳካዋለን” ይላሉ፡፡

ለዚህ ሥራ እንዲያግዝ በማሰብ ኮሜቴው የሀገረ ስብከቱን እንቅስቃሴና የምእመኑን ሁኔታ የሚያሳይ አሳዛኝና ልብ የሚነካ ፊልም አዘጋጅቶ አቅርቧል፡፡ “በእውነት በዚህ ፊልም ሐዋርያዊ ተልዕኮ ምን እንደሚመስል ይረዱበታል” የሚለው ፊልሙን የተመለከተው ዲያቆን በረከት ነው፡፡ “ምን አልባትም ቀጣዮች ቅዱሳን ከዚያ አካባቢ ይመጡ ይሆናል፣ ማን ያውቃል?” በማለት ራሱን የሚጠይቀው ዲየቆን በረከት የምእመኑ ንፁህ እምነትና የዋህነት ልቡን የነካው ይመስላል፡፡

በዋነኝነት ግን ትኩረት ተሰጥቶ ለጊዜው የተሠራባቸውና እየተሠራባቸው ያሉ ዝግጅቶች አሉ፡፡ የመጀመሪያው ከግንቦት 24 እስከ 28/2003 ዓ.ም በቦሌ መድኃኒዓለም ቤተ ክርስቲያን ቅጽረ ግቢ ውስጥ የተዘጋጀው አውደ ርዕይ ነበር፡፡ በአውደ ርዕዩ የሀገረ ስብከቱ እንቅስቃሴዎች በሰፊው የተዳሰሱ ሲሆን ብዙ ምዕመናን ጎብኝተውታል፡፡ “እኔ ፕሮቴስታንት ነበርኩ፤ ከዛሬ ጀምሮ ግን ኦርቶዶክስ ሆኛለሁ፤ መጠመቅም እፈልጋለሁ” በማለት አንድ የፕሮቴስታንት እምነት ተከታይ አውደ ርዕዩን በማየት የተመለሰበት ሁኔታ ነበር፡፡  

እነዚህን ወገኖቻችን ለመታደግ ከተዘጋጁት መርሐ ግብራት ውስጥ በርካታ ምእመናን ይሳተፉበታል ተብሎ የሚጠበቀው ሰኔ 5 ቀን 2003 ዓ.ም በጠቅላይ ቤተ ክህነትና በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ አዳራሾች በተመሳሳይ ቀንና ሰዓት ይኸውም ከቀኑ 7፡00 ጀምሮ የሚደረገው ነው፡፡ ጉባኤው በአዲስ አበባ ከሚገኙ ሰ/ት/ቤቶች ኅብረት ጋር በጋራ የተዘጋጀ እንደሆነ ታውቁል፡፡

ይህ ጉባኤ የኢንተርኔትን ቴክኖሎጂ በመጠቀም በመላው ዓለም እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ሊሠራጭ የሚችልበት እድል እንደሚኖር አስተባባሪ ኮሜቴው ይገልጻል፡፡

የኢትዮጵያ ቤተ ክርስትያን ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ባለ እዳ ብትሆንም ገና ያላስተማረቻቸውና ያላጠመቀቻቸው በሥሯ ብዙ ምዕመናን አሉ፡፡ እነርሱም ሁሌ ጡት እንደሚፈልግ ሕፃን እጃቸውን ይልካሉ፣ እናቱ እንደጠፋችበት ሕፃን በር በሩን ይመለከታሉ፡፡ መቼ ይሆን የምንደርስላቸው? በእንደዚህ ዓይነት ጉባኤያት? ምን አልባትም አንዱ ሊሆን ይችላል፡፡

በማኅበረ ቅዱሳን የኅትመት ውጤቶች ላይ ተጥሎ የነበረው የአባ ሠረቀ ሕገ ወጥ ደብዳቤ ተሻረ

ተ/ሥላሴ ጸጋ ኪሮስ
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሓላፊ ቆሞስ አባ ሠረቀ ብርሃን ወልደ ሣሙኤል ማኅበረ ቅዱሳን የሚያሳትማቸው መጽሔትና ጋዜጣ ለኅትመት እንዳይውሉ የጻፉት ሕገ ወጥ የእግድ ደብዳቤ እንዲነሣ መደረጉን የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት አስታወቀ፡፡

በጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ፊርማ በቀን 01/10/2003 ዓ.ም ተጽፎ ለሚመለከታቸው አካላት የተሠራጨው ደብዳቤ እንዳመለከተው የማኅበረ ቅዱሳንና የመምሪያው ጉዳይ በወርኃ ግንቦት በተደረገው የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ላይ በአጀንዳነት ቀርቦ ችግሩን ለዘለቄታው ለመፍታት አጣሪ ኮሚቴ ተሰይሞ ባለበት ሁኔታ የመምሪያው ሓላፊ ሕገ ወጥ የእግድ ደብዳቤ መጻፉ አግባብ አይደለም ይላል፡፡

ማኅበሩ እገዳው አግባብ አለመሆኑን ለሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ ባቀረበው አቤቱታ ገልጿል።

ብፁዕነታቸው ለጠቅላይ ጽ/ቤቱ በቀን 29/09/2003 ዓ.ም በጻፉት ደብዳቤ «የመምሪያው ሓላፊ የማኅበሩ መጽሔትና ጋዜጣ ኅትመት ላይ እንዳይውሉ በማለት ለተለያዩ ማተሚያ ድርጅቶችና ብሮድካስት ባለሥልጣን መጻፉን አመልክቶ፥ የሰ/ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያና የማኅበረ ቅዱሳን ጉዳይ በአጀንዳነት ቀርቦ ችግሩን በዘለቄታው ለመፍታት ያስችል ዘንድ ጉዳዩን አጥንቶ የሚያቀርብ ከብፁዓን አበውና ከሊቃውንቱ የተውጣጡ አባላት ያሉት ኮሚቴ ተቋቁሞ ባለበት ወቅት ይህ የእግድ ደብዳቤ መጻፉ አስፈላጊ ነው ብዬ ባላምንም ከእኔ በላይ ሆኖ ስላገኘሁት ይህንኑ ጉዳይ ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ በትኩረት ተመልክቶ መፍትሔ እንዲሰጥበት» ማለታቸውን ተጠቅሷል፡፡

ይህንን የማደራጃ መምሪያውን የበላይ ሊቀ ጳጳስ ማሳሰቢያ ተከትሎም «የመጽሔትና ጋዜጣ ሕትመት እገዳው እንዲነሳ የተደረገ መሆኑን እናሳውቃለን» የሚለው የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ደብዳቤ ነው። በተጨማሪም በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሥር ስላለ የማኅበረ ቅዱሳን ሥራ እንቅስቃሴ ጉዳይ ተጣርቶ የሚያቀርብ ብፁዓን አባቶች ያሉበት ኮሚቴ ተሰይሞ ሥራውን ለመጀመር በዝግጅት ላይ ባለበት ወቅት ንትርክና ጭቅጭቅ መፈጠሩ የማጣራቱ ሥራ ሒደት ላይ እንቅፋት ሊፈጠር እንደሚችል ጠቁሟል፡፡

ይኸው የእገዳ ደብዳቤ እንደተነሣ ለብሮድካስት ባለሥልጣን እና ለሌሎች ስድስት ማተሚያ ቤቶች የተጻፈ ሲሆን ሌሎች የሚመለከታቸው አካላትም በግልባጭ እንዲደርሳቸው ተደርጓል፡፡

 
የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሓላፊ ቆሞስ አባ ሠረቀ ብርሃን ወልደ ሣሙኤል በጻፉት ተገቢ ያልሆነ የእገዳ ደብዳቤ ባለፈው ቅዳሜ ለኅትመት ገብታ የነበረችው 18ኛ ዓመት ቁጥር 18 ቅጽ 18 ቁጥር 226 /ከሰኔ 1 እስከ 15 ቀን 2003 ዓ.ም/ እትም ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ የኅትመት ጊዜዋ እንደተስተጓጎለ ታውቋል፡፡

ይሁንና ጋዜጣው በትናንትናው ዕለት ማለትም ግንቦት 30 ቀን 2003 ዓ.ም ለኅትመት በቅታ ምእመናን ዘንድ ደርሳለች፡፡

በቤተ ክርስቲያኗ መዋቅር ሥር ሆኖ በሚንቀሳቀሰው ማኅበረ ቅዱሳን አሳታሚነት ኅትመቷን ከጳጉሜን 5 ቀን 1985 ዓ.ም የጀመረችው ስምዐ ጽድቅ ለአንድም ዘመን ኅትመቷ ሳይስተጓጎል ምእመናንን ትምህርተ ሃይማኖትን በማስተማር፣ እምነትን በማጽናት፣ መናፍቃንንና አጽራረ ቤተ ክርስቲያንን በማጋለጥ፣ መንፈሳዊና ማኅበራዊ ጉዳዮችን በመዳሰስ ስታበረታና ስታጽናና እንደቆየች ይታወቃል፡፡ 

ለማስተጓጎል ተሞክሮ የነበረው የስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ እትም ስርጭት ላይ ዋለ።

ተ/ሥላሴ ጸጋ ኪሮስ
ለማተሚያ ድርጅቶች በተፃፈ አግባብነት የሌለውና መዋቅሩን ያልጠበቀ ደብዳቤ ለማስተጓጎል ተሞክሮ የነበረው የስምዐ ጽድቅ 18ኛ ዓመት ቁጥር 18 እትም ታትሞ መውጣቱ ተገለጸ። ህትመቱም ስርጭት ላይ ነው።

የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ኃላፊ አባ ሠረቀ ብርሃን ወልደ ሣሙኤል ለማተሚያ ቤቶች በፃፉት ደብዳቤ “የማኅበሩ መጽሔት ጋዜጣ በእናንተ በኩል ኅትመት ላይ እንዳይውሉ” በማለት ጠይቀው ነበር።

የማደራጃ መምሪያ የበላይ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ በበኩላቸው ይህ የማደራጃ መምሪያው ኃላፊ ደብዳቤ ህጋዊ እንዳልሆነ ለጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት በጻፉት ደብዳቤ አሳስበዋል። ይህንን ተከትሎ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ለማተሚያ ቤቶች የተፃፈውን አግባብነት የሌለው ደብዳቤ ለማንሣት ይጽፋሉ ተብሎ ይጠበቃል።

ማኅበሩ ያሉትን ሚዲያዎች በተመለከተ ከሚመለከታቸው የጠቅላይ ቤተ ክህነት አካላት ጋር ለመስራት ምክክር ከጀመረ ቆይቷል ሲሉ የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ ሊቀ ትጉሃን ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ስዩም ለአማርኛ መካነ ድር ገልጸዋል።

ቅዱስ ሲኖዶስ በግንቦቱ የርክበ ካህናት ምልዓተ ጉባኤ አጣሪ ኮሚቴ ሠይሞ የማኅበረ ቅዱሳንንና የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያን ጉዳይ ለማየት በወሰነበት ውቅት ይሄንን ደብዳቤ መጻፋቸው እንዲህም ለተለያዩ ሚዲያዎች መግለጫ መስጠታቸው ብዙዎችን ያነጋገረ ጉዳይ መሆኑ ይታወሳል።

 

capital C

Capital “C”

በድንቅነሽ ጸጋዬ

ሰኔ 1/2003 ዓ.ም.     

capital C

 
ዛሬ ደግሞ እንደ ሙአለ ሕፃናት ተማሪዎች Capital “C”ን እዚህ ምን አመጣት ትሉኝ ይሆናል፡፡ እኔም የትኩረት አቅጣጫዬ ስለ Capital “C” እንዳልሆነ እርግጠኛ ነኝ፡፡ ስለ ትምህርት ሲነሣ ወላጆቻችን ሀ ብለው የጀመሩት በተለምዶ ቄስ ትምህርት ቤት ብለን በምንጠራቸው ሲሆን፥ ትምህርቱም ይሰጥ የነበረው የሁሉም አፍ መፈቻ ቋንቋ ባይሆንም አብዛኛው ሰው ይግባበት በነበረው የአማርኛ ቋንቋ ፊደል ሀሁ፣ አቡጊዳ፣ መልዕክተ ዮሐንስ ዳዊት…ወዘተ፥ ዘመናዊውን የአስኳላ ትምህርት ከመቀጠላቸው በፊት፥ እንደተማሩ እናውቃለን፡፡ ለዚህም ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ዋነኛ የትምህርት ማዕከል ሆና አገልግላለች፡፡
ስማቸው በዓለም አቀፍ ደረጃ የገነነው የእንግሊዙ “ኦክስፎርድ” እና የአሜሪካው “ሃርቫርድ” ስመ ጥር ዩኒቨርሲቲዎች መነሻቸው ከቤተ ክርስቲያን ነበር፡፡ በዛሬው አኳኋን ተደራጅተውና በዘመናዊ ትምህርት ተውጠው ከመገኘታቸው በፊት የሃይማኖት ትምህርት ማሰልጠኛ ማዕከላት ነበሩ /የካቶሊክም ቢሆኑ/፡፡ ከዚህ የምንማረው ቁም ነገር፥ ዓለም ለደረሰበት የሥልጣኔ ቁንጮ የመድረስ ዋዜማውና መፍትሔው በሌሎች ላይ መንጠልጠል ሳይሆን በነባሩ /የራስ/ እሴት መሠረትነት ላይ ማነጹ እንደሆነ ነው፡፡ ለረጅም ዘመናት አገራችንን የመሩት ምሁራን ነገሥታቱና በየሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ የነበሩ ቁልፍ ሰዎች መገኛቸው የቤተ ክርስቲያን ትምህርት እንደነበርም አይካድም፡፡
 
የተለያዩ ጥናቶች እንደሚያመለክቱት፥ በየትኛውም አገር ተማሪዎች በአፍ መፍቻ ቋንቋቸው ሲማሩ ለትምህርት ያላቸው ፍላጎትና ተቀባይነት ብሎም የመረዳት ደረጃ ፈጣን ይሆናል፡፡ ከዚህም ባሻገር ለቋንቋው እድገትና ተተኪ ለማፍራት የሚያደርገው አስተዋጽኦ ቀላል አይሆንም፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስም ለአፍ መፍቻ ቋንቋ ትልቅ ቦታ ተሰጥቶት እናገኛዋለን፡፡ የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ወንጌል በመጀመሪያ የተጻፈው ወንጌላውያኑ እንደተሰማሩበት የስብከት ቋንቋ፥ ቅዱስ ማቴዎስ በምድረ ፍልስጥኤም በዕብራይስጥ፤ ቅዱስ ማርቆስ ለሮማውያን በሮማይስጥ፤ ቅዱስ ሉቃስ ለመቄዶንያ በጽርዕ እና ቅዱስ ዮሐንስ ለኤፌሶን በዮናናውያን ቋንቋዎች መሆኑን እንረዳለን፡፡
በተጨማሪም ሐዋ.2÷1 እንደምናገኘው ቅዱሳን ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስ በገለጠላቸው 72 ቋንቋዎች ከተለያየ ሀገር ለበዓል የተሰበሰቡትን ሕዝቦች በየሀገራቸው ቋንቋ ወንጌልን ስላስተማሯቸው በዕለቱ 3000 ሰዎች አምነው ተጠምቀዋል፡፡ ይህም ሰው በአፍ መፍቻ ቋንቋው ሲማር ለመረዳት እና ወደ ተግባር ለመለወጥ ፈጣን እንደሆነ ያረጋግጥልናል፡፡

ሐዋርያዊት እና ዓለም አቀፋዊት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንም ለአፍ መፍቻ ቋንቋ ትኩረት በመስጠት ሁሉም ወንጌልን ተምረው ከሥላሴ ልጅነትን አግኝተው መንግሥተ እግዚአብሔርን እንዲወርሱ ባላት አቅም በሁሉም አህጉረ ስብከቶች በመተግበር ላይ ትገኛለች፡፡ እኛስ ልጆቻችንን እንዴት እያስተማርናቸው ነው? በአፍ መፍቻ ቋንቋቸው? ቢያንስ ከሀገርኛ ቋንቋዎች በአንዱ? ወይስ ጥሩ እንግሊዝኛ ቋንቋ ተናጋሪ እንዲሁኑ ከማሰብ? አብዛኛው ባለሀብትም/የትምህርት ቤት ባለቤቶች/ የወላጆች አስተሳሰብ ስለገባቸው ደረጃውን ባይጠብቅም የትምህርት ቤቱ ስም በእንግሊዝኛ ሲሆን ኢንተርናሽናል የሚል ተጨምሮበት፣ ማስታወቂያቸው በውጭ ዜጋ መሆን ከጀመረ ሰንብቷል፡፡ ልክ ነዋ! በአገርኛ ቢጻፍ ማን ትኩረት ይሰጠዋል፡፡

ልጆቻችን በአፍ መፍቻቸው እየተማሩ ሌሎች የሀገራችንንም ሆነ የውጭ ቋንቋዎች ቢችሉ አይጠቅምም ባይ አይደለሁም፡፡ በአሁኑ ጊዜ እየሆነ ያለው ግን “የራስን ጥሎ” በአብዛኛው ትምህርት የሚጀምሩበት ቋንቋ እንግሊዘኛ መሆኑ ነው፡፡ ታዲያ ምን ችግር አለው የሚል አይጠፋም! ከአመታት በፊት የወንድሜን ልጆች ት/ቤት ልናደርስ እየሄድን የያዝኩትን መፍሔት ተቀብላ በፍጥነት Capital “C” አለችኝ፤ “ሐመር” ከሚለው ውስጥ “ር”ን ነጥላ በጣቷ እያመለከተችኝ፡፡ “ሐ” እና “መ”ን ግን እንደማታውቃቸው ስትገልጽልኝ በጣም ባዝንም አልፈረድኩባትም፡፡ A-for Apple, B-for Banana…. አየተባለች እንጂ በአፍ መፍቻዋ ፊደል እንድትቆጥር ከቤተሰብም ሆነ ከትምህርት ቤት እድል አላገኘችም፡፡ በአሁኑ ሰዓት የ7ኛ ክፍል ተማሪ ብትሆንም የአማርኛ ውጤቷ እንደሌላው ትምህርት የሚደነቅ አይደለም፡፡ ታናሽ ወንድሟም ቢሆን የዚሁ ችግር ተጠቂ ስለሆነ በጥናት ወቅት የአባቱን እርዳታ የሚጠይቀው የአፍ መፍቻ ቋንቋው ለሆነው ነገር ግን ብዙም ለማይረዳው ለአማርኛ ነው፡፡ አንድ ቀን ነው “አባቢ ሐረግ ምን ማለት ነው?” አለው፡፡ አባትም የቻለውን ያህል ገለጸለትና በደንብ የተረዳ ስላልመሰለው በእንግሊዘኛ “Phrase እንደማለት” ሲለው ፈገግ ብሎ “ነው እንዴ” አለ! ይገርማል አማርኛን ለማስረዳት በእንግሊዝኛ ተተርጉሞ ማለት ነው፡፡
ሌላ ልጨምርላችሁ በመዲናችን ውስጥ ካሉ ስመ ጥር ኢንተርናሽናል ትምህርት ቤቶች በአንዱ የ5ኛ ክፍል መምህርት ጓደኛ አለችኝ፡፡ ተምሮ መፈተን፥ አስተምሮ መፈተን ያለነውና አማርኛ ትምህርት ልትፈትን ወደ ክፍል ዘለቀች ከተማሪዎቹ አንዱ ፈተናውን ተቀብሎ ”ጀምሩ“ ሲባል “ሚስ አልፈተንም” ብሎ እርፍ፡፡ “ለምን?” ሚስ ጠየቀች “አስኪ ተመልከችው ስትራክቸሩ /የፊደሉ ቅርጽ/ ሲያስጠላ” አላት፡፡ በዚህ አቋሙ በመጽናቱ ሚስም ሳታነብ፣ እሱም ሳይፈተን ቀረላችሁ፡፡
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ “የአማርኛ ፊደላት በዝተዋልና ይቀነሱ” የሚሉ አስተየየቶች መነሣታቸውን አስታውሳለሁ፡፡ ዛሬ የፊደል ቅርጻቸው ያስጠላል ያሉን ሕፃናት ነገ ከነጭራሹ አያስፈልጉንም ላለማለታቸው ምን ያህል እርግጠኞች ነን? ቅኝ ብንገዛ ኖሮ እንግሊዝኛ እንችል ነበር ብለው በቁጭት የሚናገሩ ወገኖች እንዳሉም ባይዘነጋ፡፡ ይህን ሲሉ ግን ጣሊያን በኢትዮጵያ በነበረችባቸው አምስት ዓመታት ውስጥ አንድም ጣልያንኛ ቃል ያላወቁትን አስተውለዋል? አሁንስ ቢሆን በተዘዋዋሪ የአስተሳሰብ ቅኝ ተገዢዎች መሆናቸውንስ?
የዛሬ ሕፃናት የነገ ሀገር ተረካቢዎች መሆናቸው ለማንም ግልጽ ነው፡፡ የሀገራችን ባሕል ታሪክ እና የማንነታችን መገለጫ መዛግብቱ የተጻፉት ደግሞ በግዕዝ፣ በአማርኛ እና በሌሎች የብሔር ብሔረሰብ ቋንቋዎች መሆኑ ይታወቃል፡፡ ታዲያ ሕፃናቱ የሀገራቸውን ባሕል፣ ታሪክ ማንነት ለመረዳት በውጭ ቋንቋ ተተርጉሞ ካልመጣ ላያነቡ ነው? ስለ እኛ በውጭ ቋንቋዎች የተጻፉትስ ምን ያህል ሚዛናዊ ሆነው ማንነታችንን ይገልጻሉ?
በሀገር ውስጥ ካሉ ሕፃናት ይህን ከተመለከትን በውጭ የኑሮ ውጥረት በበዛበት ቤተሰብ ተከታትሎ ባሕላቸውን፣ ታሪካቸውን በአጠቃላይ ማንነታቸውን እየተነገሩ ያላደጉ ሕፃናት እንዴት ይሆኑ? ይህን ስል ግን ባላቸው የተጣበበ ሰዓት በየቤታቸው እና በየአብያተ ክርስቲያናቱ ፊደል የሚያሰቆጥሩ ባሕላቸውና ታሪካቸውን የሚያስተምሩ መኖራቸውን ሳልዘነጋ ነው፡፡
ሐሳቤን ለማጠቃለል ያህል ወላጆችስ ይህ ጉዳይ አሳስቦን ያውቃል? ወይስ ጥሩ የውጭ ቋንቋ ስለተናገሩልን በቃ የዕውቀት ዳር የደረሱልን መስሎን ዝም ብለን ተቀምጠናል? የሚረከቧትን ሀገር ታሪክ፣ ባሕልና ማንነት የማያቁ ተተኪዎች እያፈራን መሆናችንንስ አስበነው እናውቃለን? እኔ ግን “ር”ን Capital “C” ስትለኝ በሁኔታው አዝኜ ዝም ባልል ኖሮ “ዘ”ን ኤች፣ “ረ”ን ኤል፣ “ጠ”ን ስሞል ኤም፣ “ዐ”ን ኦ፣ “ተ”ን ስሞል ቲ፣ “ሀ”ን ዩ፣ “ሠ”ን ደብልዩ ወዘተ ልትለኝ እንደምትችል አልጠራጠርም፡፡