የደቡብ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ከምእመናን ጋር ተወያዩ።

በተ/ሥላሴ ጸጋ ኪሮስ

በሐዋሳ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን የተነሳው አለመግባባት አሁንም ቀጥሎ ማክሰኞ በ08/06/03 ዓ.ም በቤተ ክርስቲያን ውስጥ በተፈጠረው ግጭት ወጣቶችና ምእመናን ጉዳት ደርሶባቸዋል። እርሱን ተከትሎ ያለመግባባቱን ተዋናዮች ሰብስበው ያናገሩት የደቡብ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ክቡር አቶ ሽፈራው ሽጉጤ ተቃውሞን ሰላማዊ በሆነ መልኩ ብቻ መግለጥ እንደሚቻል አሳስበዋል።
 
በግጭቱ ወቅት በስፍራው እንደተገኙ የተናገሩ የዐይን ምስክር “በቤተ ክርስቲያን ውስጥ በሁለት ጎራ ተለይቶ ጉባኤ ከተጀመረ ቆይቷል።” ብለው፤ ስለ ዕለቱ ክስተት ሲናገሩ “በአንደኛው ወገን የተወሰኑ ሰዎች ለጸሎት ተሰብስበው እያሉ ከቀኑ 9፡30 ሲሆን፥ ከሌላኛው ወገን በትር ይዘው በመምጣት ሁለት ልጆችን በተደጋጋሚ ሲደበድቧቸው፤ ሌላ አንዲት ምእመን ግንባሯ ላይ ተፈንክታ እንደተመለከቱ ገልጸዋል።

ከዚህ አለመግባባትና ግጭት በኋላ ከሁለቱም ወገን የተወከሉ ሃምሳ ሃምሳ ሰዎችና የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ገብርኤል በተገኙበት ከክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ክቡር አቶ ሽፈራው ሽጉጤ ጋር ውይይት ተካሂዷል። በውይይቱ ወቅት ሁለቱም ያላቸው ሃሳብና ቅሬታ አቅርበዋል።

በአንደኛው ወገን የአለመግባባቶቹ መነሻና ሂደቶቹ የቀረቡ ሲሆን፥ በሌላኛው በኩል በአብዛኛው ሲነገሩ የነበሩት የማኅበረ ቅዱሳንን ጣልቃ ገብነት፥ እንዲሁም ማኅበሩን የመክሰስ ሁኔታዎች እንደነበር ምንጮቻችን ገልጸዋል።

ክቡር ርዕሰ መስተዳድሩ በውይይቱ ወቅት አጽንኦት ሠጥተው የገለጹት ነገር፥ ከእንግዲህ አንዲት ጠጠር በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እንደማትወረወርና ማንኛውንም ተቃውሞ ሰላማዊ በሆነ መልኩ መግለጥ እንደሚቻል ነው።

አቶ ሽፈራው አያይዘውም “ሊቀ ጳጳሱ እዚህ ቦታ እስከተቀመጡ ድረስ በሀገረ ስብከታቸው የሊቀ ጳጳሱ ወሳኔ የቤተ ክርስቲያኒቱ የመጨረሻ ውሳኔ ነው፤ እርሱን ተቀብለን እንሄዳለን” በማለት አብራርተዋል።  

መነሻው ከ9 ወር በፊት አካባቢ እንደሆነ የሚነገርለት አለመግባባት፥ ቀኖና ቤተ ክርስቲያን ይጠበቅ፣ የቃለ ዓዋዲው መመሪያ ይከበር፣ የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ተግባራዊ ሊሆን ይገባል፤ በሚሉና ይህንን በሚቃወሙ መካከል እንደሆነ የሲዳማ፣ አማሮና ቡርጅ ልዩ ዞኖችና ወረዳዎች ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ኅሩያን ዓለም እሸት ገ/ጻድቅ ከማኅበረ ቅዱሳን የአማርኛ መካነ ድር ጋር ባደረጉት ቆይታ መግለጻቸው ይታወሳል።

hawassakidusgebrieltiks.jpg

“የእኛ ግዴታ ሲኖዶስ ያወጣውን ሕግ ማስከበር ነው” ሊቀ ኅሩያን ዓለም እሸት ገ/ጻድቅ

በተ/ሥላሴ ጸጋ ኪሮስ   

hawassakidusgebrieltiks.jpgባለፈው ጊዜ በሐዋሳ ከተማ በተለይም ደብረ ምሕረት ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን የተፈጠሩትን ጉዳዮች አስመልክቶ ከሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ኅሩያን ዓለም እሸት ገ/ጻድቅ ጋር ያደረግነውን ውይይት የመጀመሪያ ክፍል የሐዋሳ ጉዳይ 1 በሚል ርዕስ አቅርበንላችሁ ነበር። የውይይታችን ቀጣይ ክፍል ደግሞ እነሆ፤ መልካም ንባብ። (ፎቶ፦ ሐዋሳ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ግቢ ውስጥ ከሚገኙት ጥቅሶች መካከል)

•    በብፁዕነታቸው መልካም ፈቃድና በሀገረ ስብከቱ ጥረት እርቅ እንደተካሄደ ይታወቃል። የእርቁ ሂደት እንዴት ነው? ከእርቁ በኋላ አለመግባባቶች እንዴት ሊፈጠሩ ቻሉ?

እንግዲህ በኛ በኩል እርቁ አልፈረሰም እንደተጠበቀና እንዳለ ነው፡፡ የዕርቅ ስምምነት የተባለው፤ የተጣላ ኖሮ አንተ ይህን አድርገሀል አንተ ይህን አድርገሀል ተብሎ እርስ በእርሱ የተጣላ ኖሮ አይደለም። ዋናው የቤተ ክርስቲያኒቱ መመሪያና ደንብ አልተከበረም ነው፡፡ ይህንን በሚመለከት በመንግሥት አካላት በኩልም የቤተ ክርስቲያኒቱን ደንብና መመሪያ እንዲያውቁት፥ ግንዛቤ እንዲኖር፥ በታዛቢነትም ተገኘተው ደግሞ የራሳቸውን ሀሳብና አስተያየት እንዲለግሱን አድርገናል። ይህን ከማድረግ አኳያ ከሁሉም የኅብረተሰብ ክፍል ማለትም ከአገር ሽማግሌዎች፣ ከሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች፣ ከሰበካው ጉባኤውና ከልማት ኮሚቴ ከሚመለከታቸው ክፍሎች ሁሉ የተውጣጡ አካላት ባሉበት፥ ከመንግሥት አካላትም በታዛቢነት አድርገን ባለ ሰባት ነጥብ የያዘ የእርቅ ሰነድ ወይም ውሳኔ የሚባለውን ያዘጋጀነው፡፡

ውሳኔውና የእርቅ ሰነዱ ብዙ ነገሮች ሲኖሩት ሌላው ሁሉ እንዳለ ሆኖ፥ ጠቅለል ባለ መልክ ሁሉም ነገር በቃለ አዋዲው እና በቤተ ክርስቲያኒቱ ሕግና መመሪያ መሠረት እንዲሠራ የሚል ነው፡፡ በተለይ ደግሞ በእርቅ ሰነዱ ሰባተኛው እና የመጨረሻው ተራ ቁጥር ላይ ሰባክያንና ዘማርያንን የተመለከተ ነው፤ አብዛኛውን ጊዜ ችግር የሚያመጣውና አለመግባባት የሚያስከትለው ጉዳይ እሱ ነው፡፡ ምክንያቱም ሰዎች ይነሳሱና እነ እከሌ መስበክ አለባቸው ይላሉ፡፡ የቤተ ክርስቲያኒቱ አስተዳደርና አካሄድ ደግሞ ይህን አይፈልግም፥ ስለዚህ አሁን እገሌ ይስበክ እገሌ አይስበክ ሳይሆን፥ የሚሰብክ ሰው በቤተ ክህነቱ ሕጋዊ እውቅና ኖሮት ይስበክ የሚል ነው፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ ምሳሌው አይሄድም እንጂ ፈቃድ ሲባል እንደ ንግድ ፈቃድ ወይም እንደ ቀበሌ መታወቂያ አንድ ጊዜ የሚሰጥ አይደለም። አንድ ጉባኤ፣ ክብረ በዓል ሲኖር ወይም ወደ አንድ ቦታ ላይ ተጉዞ የወንጌል ማስተማር ጉባኤም ካለ፥ ለዚያ ጉባኤ እገሌ የተባለ ሰባኬ ወንጌል ወይም መምህር እንዲያስተምር የሚል ደብደቤ መኖር አለበት ነው፡፡ ያን ደብዳቤ የሚጽፈው ደግሞ በጠቅላይ ቤተ ክህነት የስብከተ ወንጌል እና ሐዋርያዊ ተልዕኮ መምሪያ ወይም ደግሞ የሀገረ ስብከቱ ጽሕፈት ቤቱ ሊሆን ይችላል። በዚህ መልኩ ነው ሥራው መሠራት ያለበት፡፡ እነዚህን የመሳሰሉት ውሳኔዎች በእርቅ ሰነዱ ላይ ተካተው ከክልሉ መስተዳድር ጀምሮ ለሚመለከታቸው የመንግሥት አካላት ተላልፏል፤ የመንግሥት አካላትም በታዛቢነት በተገኙበት ሕጉን አስረግጠን ነግረን በግልጽ በጉባኤ ተነቧል። በተለይም ሰባክያንን፣ ዘማርያንን፣ ባሕታውያንንና የመሳሰሉትን በሚመለከት ቅድም እንዳልኩት በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ፊርማ ለመላው አህጉረ ስብከት የተላለፈው መመሪያ በሚገባ ተነብቦ፣ ተገለጾ፣ ታይቶ መመሪያው ተጠብቆ በሲኖዶስ ውሳኔ መሠረት እንዲሠራ፤ እንዲሁም በተለይ በሀገረ ስብከቱ ክልል ባሉ አብያተ ክርስቲያናት ከጠቅላይ ቤተ ክህነት ወይም ከሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ያልተፈቀደለት አካል በቤተ ክርስቲያኒቱ አውደ ምሕረት ሲቆም ሀገረ ስብከቱ ጥብቅ ቁጥጥር እንዲያደርግ የሚል ሰፍሯል። ስለዚህ የእኛ ትግል የሲኖዶስን መመሪያ ተግባራዊ ለማድረግ ነው ማለት ነው። በዚያ መሠረት ነው የምንሠራው። የእርቅ ሰነዱ ውሳኔ ከተላለፈ በኋላም ምንም ዓይነት ጭቅጭቅም ሁከትም አልነበረም።

ከጊዜ በኋላ እንግዲህ አሁንም ሰዎች እነ እገሌ የሚባሉት ሰባክያን ይምጡ፣ ዘማርያን ይምጡ፣ እነ እገሌ ይምጡ ማለት ጀመሩ። ቤተ ክህነቱ ደግሞ በሕጋዊ መንገድ ፈቅዶ የሚልካቸው መምህራንና ሰባኪያን አሉ፡፡ ሰዎችን ይምጡልን ቢሉም ቤተ  ክህነቱ ደግሞ እኔ እነዚህን ነው የማሰማራው ብሎ ልኳል፡፡ ሀገረ ስብከቱ እንደ ተዋረድ ከጠቅላይ ቤተ ክህነት የሚተላለፍለትን መመሪያ የመፈፀምና የማስፈጸም ግዴታ አለበት፡፡ ይሄ ለምን ሆነ? ይሄ አይሆንም ማለት ሕጉም ሥርዓቱም አያስኬድም። በዚህ ምክንያት እንግዲህ እነ እገሌ ካልሰበኩ ወይም እኛ ካልሰበክን በሚል አንዳንድ ሰዎች ተነሥተዋል፡፡ ያው እነዚያ በግል ማለት ነው፡፡ አሁንም ግን የመላው ምእመንና ካህናቱ አመለካከት የውሳኔ ሰነዱ፣ ቃለ ዐዋዲው ይከበር፤ ለሀገረ ስብከቱ አቅርቦ ሲፈቀድለት ይሰማራ ነው፡፡ ይሄንን ሳያቀርቡ ደግሞ እራሳችንን እናሰማራ የሚሉ ክፍሎች ሲነሱ፤ ይሄ አይሆንም፥ ይሄ መደረግ የለበትም በሚል ነው አለመግባባቱ የተፈጠረው፡፡ ከዚህ አንጻር ነው እንጂ እርቅ የፈረሰ ነገር የለም እርቁም ደግሞ የቤተክርስቲያኒቱን መመሪያ ጠብቀን እንሂድ፤ ሁላችንም ለቤተ ክርስቲያንቱ መመሪያ ተገዥ እንሁን የሚል ውሳኔ ነው እንጂ እገሌና እገሌ ተጣልተው የሚል የግል ጥላቻ በዚህ ላይ የለውም፡፡ የቤተ ክርስቲያንኒቱን መመሪያ ግን በጋራ እናክብር፡፡ መንግሥትም መመሪያውንም ውሳኔውንም አውቆታል፤ ይሄ ውሳኔ ለብፁዕ ቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽ/ቤት፣ ለጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት፣ በጠቅላይ ቤተ ክህነት የስብከተ ወንጌልና ሐዋሪያዊ ተልእኮ መምሪያ በግልባጭ ደርሷል። በቃ ያንኑ የነበረውን መመሪያና ሕጉን የሚያጸና እንጂ የተለያየ ነገር የለውም። ይሄ ከተባለ በኋላ ግን አሁንም ሰዎች እንደግል ፍላጎታቸው እንዲህ ካልሆነ የሚሉ ሲነሱ አይ ይሄማ ከሕግ ውጪ ነው የሚል ነው ያለው ማለት ነው እንጂ የእርቅ መፍረስ አይደለም።

•    ታዲያ ከዚህ ውሳኔ በኋላ አለመግባባቶችና ግጭቶች አልተነሱም ብለው ያስባሉ?

እንግዲህ አንዳንድ ሰባክያን እኛ እንሰብካለን፣ እኛ እንዲህ እናደርጋለን ብለው የሚሉት አብዛኛውን ወሬው የሚወራው በውጪ ነው፡፡ አንዳንዴ ግን ያልተፈቀደላቸው ሰዎች ወይም ያልተመደቡ ሰባክያን ወይም ቤተ ክህነቱ ያላሰማራቸው ዘማርያን ሆኑ ሰባክያን ወደ ዐውደ ምሕረቱ ሲመጡ፥ የለም፤ ይሄ አይደለም፤ ይላል ምእመኑ። ምእመኑ ነው መመሪያውን የሚያስከብረው። ይሄ ሰባኪ አይደለም የተመደበው ይላል። በዚህ ጊዜ የግድ አለመግባባቶች ይመጣሉ።

ሕጉ፣ መመሪያው፣ የሲኖዶሱ ደንብ፣ ቃለ አዋዲውና ሕገ ቤተ ክርስቲያኑ በአግባቡ በሥራ ላይ ይዋል ሲባል፥ የለም እኛ በፈቀድነው መሆን አለበት የሚሉ ክፍሎች ደግሞ ከተነሱ፥ ይኼማ የቤተ ክርስቲያናችን መመሪያዋ አይደለም የሚሉ ክፍሎች ይነሳሉ። በዚህ ጊዜ መቼም የሀሳብ አለመጣጣም አለመግባባት ግድ ይከሰታል። ያን ሲሆን ደግሞ ችግር ሊፈጠር ይችላል። ነገር ግን ያው ዞሮ ዞሮ ችግሮች ሲፈጠሩ በመንፈሳዊነት ሚዛን ይታያል። እንደ ሕግ የሚታየው ደግሞ በሕግ ይታያል። በዚህ ዓይነት ታይቶ እልባት እንዲያገኝ ይደረጋል፡፡

•    በሀገረ ስብከቱ በኩል የወደፊት ዕቅዳችሁ ምንድን ነው?

እንግዲህ ለወደፊቱ እግዚአብሔር ፈቃዱ ቢሆን ከፍተኛው ሥራ ያለው ከታች ስለሆነ ያለው 13ቱንም የወረዳ ቤተ ክህነቶች በተሻለ መልኩ በተሟላ የሰው ኃይል የማጠናከር፥ ባለፈው ለወረዳ ሊቃነ ካህናት፣ ለርእሰ ከተማው አድባራት አስተዳዳሪዎችና ሰበካ ጉበኤያት በተቻለ መልኩ ትምህርታዊ ሴሚናር ለመስጠት ተሞክሯል። በቀጣይነት ደግሞ በሂደት ለእያንዳንዱ ወረዳ ቤተክህነት መርሐ ግብር ወጥቶ፥ በወረዳው ሥር ያሉ አብያተ ክርስትያናትን፣ የአብያተ ክርስቲያናት አስተዳዳሪዎችን፣ የሰበካ ጉባኤ አባላትን፣ ሰባክያነ ወንጌልና ካህናትን አሳታፊ ያደረገ፥ የቃለ ዐዋዲውን መመሪያና ሕገ ደንብ በተመለከተ፣ የቃለ ዐዋዲውን ሕግና ደንብ በማይነካ መልኩ ቤተ ክርስቲያኒቱ በልማትና ሁለንተናዊ ሥራዎች ላይ ማከናወን ያለባትና ዘመኑን የተከተለ ዘመናዊ አስተዳደርና የሥራ ሁኔታዎችን በሚመለከት፥ እንደዚሁም ደግሞ የበጀትና የሂሳብ አያያዝ፣ የንብረት ጥበቃና አመዘጋገብን፣ የቅርሶች ምዝገባንና የመሳሰሉትን ሁሉ በየጊዜው ተከታታይ ስብሰባዎችን በማድረግ ሴሚናሮችን መስጠት አስበናል።

በወረዳ ደረጃ የተሰጠው ሴሚናር በአጠቢያው ሥር ላሉ ደግሞ ካልተሰጠ ሥራው ሁለት ዓይነት ስለሚሆን በየወረዳው ሥር ያሉትን አጥቢያ ቤተ ክርስቲያናትን በየወረዳው ርእሰ ከተማ አቅም በፈቀደ መጠን ሴሚናሩ እዚያ ደርሶ ይህንን ሥልጠና መስጠት የመጀመሪያ እቅዳችን ነው፡፡

ከዚሁ ጋር ደግሞ ያው በሀገረ ስብከቱ ሥር በሚተዳደረው የደ/ታ/ቅ/ ሩፋኤል ቤተ ክርስቲያን አጠገብ የካህናት ማሠልጠኛ ትምህርት ቤት አለን። በዚህ የካህናት ማሰለጠኛ ትምህርት ቤት ያለንን በጀት በመጠቀም ካህናትን እናሠለጥናለን። የሠለጠኑት ካህናትም ወደ ነበሩበት አጥቢያ ቤተ ክርስቲያናት እየተመለሱ ምእመናኑን በስብከተ ወንጌልና በመሳሰለው ሁሉ እንዲያገለግሉ የማድረጉን ሥራ አጠናክረን እንቀጥላለን።

እንግዲህ ደቡብ ክልል ወደ 56 የሚጠጉ ብሔር ብሔረሰቦችን ያቀፈ ክልል ነው። የተለያዩ ብሔር ብሔረሰቦች ተወላጅ የሆኑ እና የየብሔረሰቡን ቋንቋ የሚናገሩ የተወሰኑ ሕፃናትን በማሰባሰብ ለማስተማር ጥረት እያደረግን ነው። ለምሳሌ አሁን 12 ያህል ህፃናት አሉን። ሀገረ ስብከቱ ከኛ ቀደም ብሎ ወደዚሁ ማሠልጠኛ አምጥቶ ትምህርት ቤት ከፍቶ፥ መንፈሳዊውን ትምህርት ማለትም ከፊደል ቆጠራ ጀመሮ እስከ ሥርዓተ ቅዳሴ ሌላም ሌላም የመሳሰሉትን መንፈሳዊ ትምህርት እያስተማረ አሁን ለዲቁና የሚያበቃ ትመህርት ተምረው የሚገኙና በቅዳሴ አገለግሎት ላይ የሚገኙ አሉ። እነዚህ ልጆች ለጊዜው ቁጥራቸው 12 ቢሆንም ይሄ 12 የሆነው ቁጥር ወደ 24 ወደ 36 ብሎም ወደ 72 እንዲያድግ ቁጥሩ እየጨመረ የሚሄድበትን መንገድ ለመፍጠር ጥረት ይደረጋል።

እነዚህ ልጆች ደግሞ ከየብሔረሰቡ የተወጣጡና የየብሔረሰቡን ቋንቋ የሚችሉ እንደ መሆናቸው መጠን ወንጌልን በየቋንቋቸው ለማስተማር ይረዳቸዋል። ኅብረተሰቡም ይቀበላቸዋል። ከመንፈሳዊው ትምህርት ጎን ለጎን ዘመናዊ ትምህርትም እየተማሩ ነው። ይሄን በሚማሩ ጊዜ አንዳንድ በጎ አድራጊዎች ከሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት ጋር በመተባበር የሚቻለውን ድጋፍ በማድረግ ቀለባቸውን፣ ልብሳቸውን የትምህርት ቁሳቁስና የመሳሰሉትን ወጪ አድርጎ ዘመናዊውን ትምህርት ያስተምራቸዋል፡፡ ከመንፈሳዊውና አለማዊው ትምህርታቸው በተጨማሪ በቅዱስ ሩፋኤል ቤተ ክርስቲያን ደግሞ በዲቁና ያገለግላሉ። ሥርዓተ ቤተክርስቲያንን፣ እንዲሁ አገለግሎትንም በኪዳንና በመሳሰለው እየተለማመዱትም ይገኛሉ ማለት ነው።

የነዚህ ልጆች ወደዚህ ማሠልጠኛ ገብቶ የማደግና የመማሩ ጉዳይ በብፁዕነታቸው ትኩረት ተሰጥቶበታል። እንግዲህ ይህን ሥልጠና ለማድረግ ቁጥራቸውንም ለመጨመር በጀት ያስፈልጋል፤ ሥራዎች ሁሌም የሚሠሩት በበጀት ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያን በጀቷ ምእመናን ናቸው፡፡ በዚሁ በሐዋሳ ያሉ አንዳንድ ምእመናን ለልጆቹ የተቻላቸውን ያህል  የሚያደርጉ አሉ። ወደፊት ደግሞ ፕሮፖዛል ቀርፀን፣ እቅድ አውጥተን፣ በጎ አድራጊዎችንም በማስተባበር፣ እርዳታ ሰጪ ክፍሎችንም በማፈላለግ ለመንቀሳቀስ አስበናል። ማኅበረ ቅዱሳንም በዚህ በኩል ይረዳናል የሚል ተስፋ አለን። እንዲሁም  ማሠልጠኛው ራሱን ችሎ እንዲንቀሳቀስ የልማት ሥራዎችን በፕሮጀክት ቀርፀን ለመሥራት አስበናል። እንዲህ ዓይነት ሥራዎችን የምናከናውነው የሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት እስከ ገጠሪቱ ቤተ ክርስቲያን ያለው በቃለ አዋዲው ድንጋጌ የሠፈረው የሥራ እንቅስቃሴ እንዳለና እንደተጠበቀ ሆኖ ማለት ነው፡፡ ያኛው እንዳለና እንደ ተጠበቀ ሆኖ ሌላው እቅዳችን ደግሞ በተለይ በቤተ ክርስትያኒቱ ተተኪ ትውልድ የመፍጠርና የመተካት፥ የዛሬው ትውልድ የነገይቱ የቤተ ክርስቲያን ተረካቢ እንዲሆን የማስቻል፥ የቤተ ክርስቲያኒቱ አገልግሉት በጥንካሬና በስፋት ቀጣይነት እንዲኖረው የማድረግ፥ ለነገይቱ ቤተ ክርስቲያን በትምህርት ሰዎችን የማዘጋጀት እና ተተኪዎችን የማፍራቱን ጉዳይ ከምንግዜውም የበለጠ አቅም በፈቀደ መጠን አጠንክረን ለመሥራት ነው፡፡

•    በመጨረሻ የሚያስተላለፋት መልእክት ካለ?

እንግዲህ በሲዳማ አማሮና ቡርጂ ልዩ ዞኖች እና ወረዳዎች ሀገረ ስብከት ለሚገኙ ለመላው ካህናትና ምእመናን በሀገረ ስብከታችን ጽ/ቤት ስም የማስተላልፈው መልእክት፤ አሁንም የቤተ ክርስትያኒቱን ሁለንተናዊ መንፈሳዊ፣ የልማት እና የሥራ እንቅስቃሴ ተባብረን ሁሉንም ለማከናወን እንድንችል መላው ምእመናን እና ካህናት የቅዱስ ሲኖዶሱን ውሳኔ እና መመሪያ፥ የቃለ አዋዲውን ድንጋጌ እና ደንብ ጠብቀን ቤተ ክርስቲያኒቱ በቅዱስ ሲኖዶስ አማካኝነት በተዋረድ በምታስተላለፍልን መሠረት ሕጓን ጠብቀን አክብረን ተባብረን እንድናገለግልና እንድናስገለግል ነው። ወደ ፊት ስብከተ ወንጌል እንዲስፋፋ፥ ሰንበት ትምህርት ቤቶች እንዲጠናከሩና ቤተ ክርስቲያናችን በልማት ልትጠናከር ያስፈልጋል።

ምእመናን ደግሞ በዕውቀታቸው በገንዘባቸውና በጉልበታቸው አብያተ ክርስቲያናትን በማስፋፋት፣ በማሳነጽና በማሠራት እንዲተጉ አሳስባለሁ። ሀገረ ስብከቱም ጠቅላላ ሥራውን የሚያከናውነው  ከካህናትና ምእመናን ጋር ነውና፥ ካህናቱም ስብከተ ወንጌልን በማስፋፋት፥ መንፈሳዊ አገለግሎትን አጠናክሮ በመቀጠልና ልማትም በቤተ ክርስቲያን እንዲስፋፋ በማድረግ ሊተጉ ይገባል። ምእመናኑ እውነት በመንገር ማሳሰብ ብቻ ነው የሚፈለጉት። በእውነት ይሄ ቀረ የማይባል ከፍተኛ ሥራ የሚሠሩ በርካታ ምእመናን አሉ። በእውነት ከተነገረና ካሳሰቡአቸው፥ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናን ለቤተ ክርስቲያናቸው ወደኋላ የሚሉበት አንድም ነገር የለም። ስለዚህ ከኛ የሚጠበቀው መንገርና ማስረዳት ብቻ ነው። እኛም የሚቻለንን ያህል እግዚአብሔር እንደፈቀደ ለማስረዳት ለመንገር እንሞክራለን። አሁንም እየነገርን እያሳሰብን ነው፤ ምዕመናኑም እየሰሙን ነው፡፡ ስለዚህ መላው ምእመናንና ካህናት ተባብረን ስብከተ ወንጌሉንም እንድናስፋፋ አብያተ ክርስቲያናቱንም በልማት እንድናጠናክር እላለሁ። የሁሉም ምእመናንና ካህናት ከሀገረ ስብከቱ ጋር መተባበር አስፈላጊ ስለሆነ እስከ አሁን ያለውን ቀና ትብብራቸውን አጠናክረው አንዲቀጥሉ በሀገረ ስብከቱ ጽ/ ቤት ስም መልእክቴን አስተላልፋለሁ፡፡

•    በእውነት ጊዜዎን ሰውተው ለሰጡን ቃለመጠይቅ በእግዚአብሔር ስም እናመሰግናለን፡፡

እንግዲህ ከመጣን አጭር ጊዜ ቢሆንም ከሞላ ጎደል ያለውንና እንዲሁም ለወደፊት ያለውንና ለመሥራት የታቀዱትን እኔ የሚቻለኝን ያህል ብያለሁ፤ ብፁዕ አባታችን አቡነ ገብርኤል ደግሞ በአባትነታቸው በሀገረ ስብከቱ ያለውን ሁኔታ አስፍተው አምልተው ከኔ የበለጠ አድርገው፥ እኔ ምናልባት ያተረፍኩትም ያጎደልኩትም ካለ የበለጠ ብፁዕነታቸው አርመው አስተካክለው አስፍተው በጥሩ ቋንቋ በጥሩ ሁኔታ ለትውልዱ በሚመች መልኩ ይገለፁታል። እኔም በሀገረ ስብከቱ ስም ምስጋናዬን አቀርባለሁ፥ እግዚአብሔር ይስጥልኝ።

ማሳሰቢያ፦ይህ ቃለ መጠይቅ የተደረገው በ30/05/2003 ዓ.ም. ነው።

hawassakidusgebriel.jpg

የሐዋሳ ጉዳይ 1

hawassakidusgebriel.jpgባለፉት ጥቂት ወራት በሐዋሳ ከተማ፥ በተለይም ደብረ ምሕረት ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን በርካታ ችግሮች ሲከሰቱ ቆይተዋል። ያለውን ሁኔታ በተመለከተ ወደ ሐዋሳ የተጓዘው ሪፖርተራችን ተሥፋሥላሴ የሀገረ ስብከቱን ሥራ አስኪያጅ፥ የዋሳ ደብረ ምሕረት ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪንና ምእመናንን አናግሮ ዘገባ አጠናቅሯል።
በመጀመሪያ ከሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ ከሊቀ ኅሩያን ዓለም እሸት ገ/ጻድቅ ጋር የተደረገውን ቃለ መጠይቅ በሁለት ክፍል እናቀርባለን። በቀጣይነት በቦታው ያለውን ዝርዝር ሁኔታ የሚመለከት ሐተታዊ ጽሑፍ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ለማስነበብ እንሞክራለን።
  • ብፁዕ አቡነ ገብርኤልም ሆነ እርስዎ ከመጣችሁ ጥቂት ጊዜያት ቢሆንም፥ በሀገረ ስብከቱ ያሉ እንቅስቃሴዎች፣ በጎ ነገሮችና ፈተናዎች ካሉ ቢገልጹልን?

እኔም ሆንኩ የሀገረ ስብከቱ ሊቀጳጳስ ብፁዕ አቡነ ገብርኤል ተመድበን ከመጣን ወደ 3 ወር የሚጠጋ ጊዜ ብቻ አስቆጥረናል፡፡ እኛ ከመምጣታችን በፊት በቦታው ላይ አንዳንድ አለመግባባቶችና ችግሮች ነበሩ፡፡ እነዚህ ችግሮች እንዳሉ ነው እኛ የመጣነው፡፡ ቢሆንም ከመጣንበት ጊዜ ጀምሮ አብዛኛውን የማረጋጋት፣ የመምከር፣ የቤተ ክርስቲያኒቱን ደንብ፣ መመሪያ፣ ሥርዓትና ሕጉን የማሳወቅ፣ ሰዎች ሁሉ ወደ በጎና ወደ ቀና አስተሳሰብ እንዲመጡ የመመለስ፣ ያልተረዱት ነገር ካለ እንዲረዱ ያላወቁት ካለ እንዲያውቁ፤ አጠቃላይ የቤተክርስቲያኒቱን ሥርዓትና ሕግ በተከተለ መልኩ መንገዶችን የማሳየት፣ የማስተካከል፣ ይሄኛው ያስኬዳል፣ ይሄኛው አያስኬድም በማለት  እየነገርንና እያስተካከልን ነው የቆየነው። ችግሮቹ ምን እንደሆኑ፥ አነሣሣቸው ምን አንደሆነ በውል ባናውቀውም ከኛ በፊት አለመግባባቶች ነበሩ፡፡ አሁን ደግሞ ከመጣንበት ጊዜ ጀምሮ ሽማግሌዎችን ካህናትን፣ ማኅበረ ምዕመናንንና፣ የሰንበት ትምህርት ቤቶች ወጣቶችንና የሚመለከታቸውን አካላት በማነጋገር በተቻለ መልኩ ችግሮች በሰላም፥ በውይይትና በመግባባት የሚፈቱበትን የተቻለውን ያህል ብዙ ጥረት አድርገናል። ከዚህም በኋላ የሀገር ሽማግሌዎችም እንዲሁ ሃሳቡን እንዲያግዙንና ድጋፍ እንዲያደርጉልን አድርገን፤ እነርሱም የሚቻላቸውን በትብብር መልክ ሰርተዋል፡፡ የመንግሥት አካላትም ጭምር በእውነት ለቤተ ክርስቲያናችን በሚያስፈልገው በማንኛውም መልኩ ከክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጀምሮ በተለያዩ በፀጥታ፣ በፖሊስ፣ በደህንነት በቀበሌም በማንኛውም ሕዝባውያንና መንግስታውያን ድርጅቶች የሚገኙ፥ ቤተክርስቲያኒቷ ሕጓ፣ ሥርዓቷ፣ ደንቧ ተጠብቆ በአግባቡ ሥራዋን እንድታከናውን፤ ከቅዱስ ሲኖዶስ በሚተላለፈው መመሪያና ውሳኔ መሠረት፥ ማንኛውም ሥራ መመሪያና ደምቡ ተጠብቆ እንዲሠራ፣ ሁሉም የሚቻላቸውን ከፍተኛ ድጋፍን እገዛ እያደረጉልን ይገኛሉ፡፡ በዚህ አይነት ነው ሥራዎችን እየሠራንም እያስተካከልን የቆየነው፡፡ እንግዲህ ከቆየታው ማነስ የተነሣ /ከመጣን አጭር ጊዜ ቢሆንም/ በተቻለ መልኩ ችግሩን ከማስወገድ አንፃር ሥራዎችን በተዋረድ እያከናወንን ነው፡፡ ከዚሁ ጎን ለጎን ደግሞ ከማኅበረ ቅዱሳን ጋር በመተባበር ወደየ ወረዳዎቹ እንቅስቄሴ በማድረግ ለየወረዳዎቹ ሊቃነ ካህናትና ለየወረዳዎቹ ቤተክህነት ኃላፊዎች እንደሁም ለርዕሰ ከተማዋ /ሐዋሳ/ አድባራት አስተዳዳሪዎች ሰባክያነ ወንጌል፣ የሰበካ ጉባኤ ሊቃነ መናብርት፣ ምክትል ሊቃነ መናብርት እንዲሁም ጸሐፊዎች በሁለቱም የብፁዕነታችን ሀገረ ስብከቶች ለሚገኙት፣ ሰበካ ጉባኤን ለማጠናከር፤ ሰንበት ትምህርት ቤትን ለማደራጀት፣ ስብከተ ወንጌልን ለማስፋፋት፣ የአሥራት በኩራትና የሰበካ ጉባኤ ክፍያዎችን ለማጠናከር በብፁዕነታቸው መሪነት የ3 ቀናት ሴሚናር አካሂደናል፡፡

  • ከመጣችሁ በኋላ ችግሮችን በመፍታት እንዳሳለፋችሁ ገልጸዋል፡፡ የችግሮቹ አካሄድ አፈጣጠር ምን እንደሆነ ሊነግሩን ይችላሉ?
በሀገረ ስብከታችን ከርዕሰ ከተማው በስተቀር ቢያንስ ከ125 በላይ አብያተ liquehiruyan.jpgክርስትያናትና 13 የወረዳ ቤተ ክህነቶች ይገኛሉ፡፡ በሌሎቹ አብያት ክርስቲያናት ምንም ዓይነት የተለየ ችግር አላጋጠመንም አልፎ አልፎ አንዳንድ ቦታዎች ቢታዩም ይሄን ያህል አይደሉም፡፡ ትልቁና ከፍተኛው ችግር አልፎ አልፎ እየተነሣ ያለው በመንበረ ጵጵስናው ርዕሰ ከተማ በሚገኘው ደብረ ምህረት ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ነው፡፡ ውሳኔዎች፣ መመሪያዎች፣ ሰርኩላሮች ከጠቅላይ ቤተ ክህነት ወደ ሃገረ ስብከቱ በተዋረድ ይመጣሉ፤ ተወረዱንም ጠብቆ ወደ አድባራትና ገዳማት ይወርዳሉ፡፡ በደብረ ምህረት ቅዱስ ገብርኤል ገዳም አስተዳዳሪና ሰበካ ጉባኤ በኩል ግን መመሪያን የመፈጸምና የማስፈጸም፥ የቃለ አዋዲውን ሕግ የመጠበቅና የማስጠበቅ፤ በአጠቃላይ ግቢውን ከሁከትና አላስፈላጊ ከሆነ ነገሮች ሁሉ የመጠበቅና የማስጠበቅ ጉዳይ የሰበካ ጉባኤ ጉዳይ ሆኖ ሳለ አባላቱና የደብሩ አስተዳዳሪ ኃላፊነታቸውን ባለመወጣታቸው ምክንያት ነው ይሄ ሁሉ ችግር እየተፈጠረ ያለው። ይሄንንም ችግር እንዲፈቱ ለአስተዳዳሪው በብጹዕነታቸው ከአንድም ሁለት ሦስቴ መመሪያ ተሰጥቷል፡፡ የሰበካ ጉባኤውንም በጋራ አሰባስበን የአቅማቸውን ቃለ ዐዋዲውን ጠብቀው እንዲሠሩ፥ ከአቅም በላይ የሆነ ነገር ሲገኝ ደግሞ ለሃገረ ስብከቱና ለመንግሥት አካላት አቅርበው እንዲያስከብሩ፣ ግቢውን እንዲያስጠብቁ፤ ተደጋጋሚ ውይይቶች የጽሑፍም ሆነ የቃል መመሪያዎች ተሰጥተዋል፤ ነገር ግን ተፈጻሚነት ሳያገኙ እየቀሩ፥ በቸልታ እየታለፈ ችግሩ ወደ አለመወገድና መድረኩ በተለያየ ጊዜ የጭቅጭቅ መድረክ እንዲሆን አድርጎታል፡፡

ከፍተኛው ይሄ ችግር የሚታየው የገዳሙ ሰንበት ት/ቤት ወጣቶች ነን በሚሉት በኩል ነው፡፡ በካህናቱም፣ በማኅበረ ምዕመናኑንም በመላው ሐዋሳ ከተማ በሚገኙ ምዕመናን በእውነት ለቤተ ክርስቲያናቸው የሚያስፈለገውን የሚያደርጉ፣ የሚታዘዙትን የሚፈጽሙ፣ ቅንነት የዋህነት ያላቸው፣ ሃይማኖታቸውን ጠብቀው ይዘው ለቤተ ክርስቲያናቸው አስፈላጊውን ሁሉ የሚፈጽሙ ናቸው፡፡ እንደ ቃለ ዓዋዲው በሰንበት ትምህርት ቤት የሚታቀፉት ከ4 ዓመት እስከ 3ዐ ዓመት ያሉ ናቸው። ነገር ግን በቅዱስ ገብርኤል ሰንበት ትምህርት ቤት ውስጥ የ4ዐ ዓመት የ5ዐ ዓመት ትልልቅ ሰዎች ሁሉ አሉ የእድሜ ገደቡም የሚመለከታቸው አይደለም። ይሄ የሚያሳየው ድርሻቸውን ለይተው አለማወቃቸው ነው ከ3ዐ ዓመት በኋላ ወደ ማኅበረ ምዕመናን ነው መቀላቀል ያለባቸው፡፡ ይህን ማድረግም የሰበካ ጉባኤው የሥራ ድርሻ ነበር፡፡ ሰንበት ትምህርት ቤት በቤተ ክርስቲያን ሊቋቋሙ ከሚገባቸው ከ13 ንዑሳን ክፍሎች ውስጥ አንድ ነው ይሄንን መፈጸም የሰበካ ጉባኤው ድርሻ ነው እኛ ከመምጣታችን በፊት እኛ ከመጣንም በኋላ ተቀላቅለው አንድ ዓይነት ትምህርት ነበር የሚሰጣቸው፡፡ ስለዚህ ድርሻዎችን የመለየት፣ መመሪያዎችን የማወቅና ነገሮችን በቅንነት የመመልከት ሁኔታው የለም፡፡

በሌላ በኩል በቅዱስ ሲኖዶስ ተወስኖ በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደሪጃ መምሪያ በኩል የሚፈጸም መመሪያ አለ፡፡ ያንን ተከትሎ መሄድ ቢቻል ምንም ዓይነት ችግር አይኖርም፡፡ ነገር ግን ሰንበት ትምህርት ቤት ነን ይላሉ ዕድሜአቸው ከጣሪያ በላይ የሆኑ በውስጣቸው አሉ፡፡ እነዚያው ክፍሎች ደግሞ የገዳሙን አውደ ምህረት ይዘን እኛ ነን መስበክ ያለብን ይላሉ፡፡ ለመስበክ ደግሞ የቤተ ክርስቲያን ዶግማ ሥርዓት ቀኖና መማር ከሊቃውንት እግር ሥር ቁጭ ብሎ መጻሕፍትን መመርመር ይገባል፤ ይህ ባልሆነበት ሁኔታ እናስተምራለን እንሰብካለን ማለቱ ደግሞ ወደ ስህተት ትምህርት ይወስዳል፡፡ በአሁኑ ወቅት ደግሞ ሰባክያነ ወንጌል ነን፣ ዘማርያን ነን፣ ባሕታውያን ነን፣ እናጠምቃለን እንዲህ እናደርጋለን የሚሉትንና የመሳሰሉትን በሚመለከት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በ2001ዓ.ም የካቲት ወር ያሳለፈውና ለመላው ስብከት ያስተላለፈው ሰርኩላር አለ፡፡ በዚያ ሰርኩላር ላይ ከመንበረ ፓትርያሪኩ ጠቅላይ ጽ/ቤት ወይም ከሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ፈቃድ ያልተሰጠው ማንም ሰው መስበክ አይችልም፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቱ በቅዱስ ሲኖዶስ የምትመራና ከቅዱስ ሲኖዶስ እስከ አጥቢያ ቤተክርስቲያን ድረስ የራሷ የሆነ አስተዳደራዊ መዋቅር ያላት በመሆኗ፥ በዚያው በመዋቅር ውስጥ ተካቶ ሕጋዊ እውቅና ኖሮት፥ በየሃገረ ስብከቱ ያለውም የየሃገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስና የሃገረ ስብከቱ ጽ/ቤት አሊያም ጠቅላይ ቤተ ክህነትም የስብከተ ወንጌል ሐዋርያዊ ተልዕኮ መምሪያው አውቆት በዚህ አይነት ነው መስበክ ያለበት ይላል መመሪያው። ይሄ መመሪያ የተላለፈው በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቃነ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ፕሬዚዳንትና የዓለም ሃይማኖቶች ለሰላም የክብር ፕሬዚዳንት ክቡር ፊርማ ተፈርሞ ነው፡፡ እኛ ደግሞ እንደ ሀገረ ስብከት በቅዱስ ሲኖዶስና ከብፁዕ ወቅዱስ አባታችን የሚሰጠውን መመሪያ የመፈፀም የማስፈጸም ኃላፊነት፣ የቤተክርስቲያን ልጅነትና አደራ አለብን፡፡

እንደ ሀገረ ስብከት ግን እገሌ ይስበክ እገሌ አይሰበክ የሚል አመለካከት የለንም፡፡ በአንዳንድ አካላት ግን እንደዚህ አይነት ሰባክያን ካልመጡልን እንደዚህ ዓይነት መምህራን ካልመጡልን የሚል የግል ጥያቃቄዎች ይነሳሉ፤ ሃሳቦቹ ለምን ኖሩ አንልም፡፡ ነገር ግን ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የሚያሰማራቸው፣ የሚቆጣጠራቸው፣ አንድ ጥፋት  ቢያጠፉ ሊጠይቃቸው የሚችል ከጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ጀምሮ እስከ ገጠሪቱ ቤተ ክርስቲያን ድረስ በቤተ ክርስቲያኒቱ የአስተዳደርን የሥራ መዋቅር ውስጥ የተካተቱ ሊሆን ይገባል፡፡ ደግሞም በርካታ ሠራተኞችና ሊቃውንት አሏት፡፡

እናስተምራለን ለሚሉ ግን ለጠቅላይ ቤተ ክህነት ወይም ለሃገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ መጠየቂያ ቀርቦ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልዕኮ መምሪያ ጉዳዩን መርምሮና አጣርቶ፥ ይህ ሰው ብቁ ነው ብቁ አይደለም፥ ለማስተማር አስፈላጊውን የትምህርት ሆኔታ ይዟል አልያዘም፥ የሚለውን ሁሉ አይቶ ሲያሰማራ /ሲፈቀድ/ ሊሆን ይችላል፡፡

ለምሳሌ አንድ ሰው በራሱ ተነሳሽነት ተነስቶ ወይ ባሕታዊ ነኝ ወይም ሰባኪ ነኝ ብሎ አንድ አጥቢያ ቤተክርስቲያን ላይ እሰብካለሁ ቢል፡-
1.    የደብሩ አስተዳዳሪ ወይም ሰበካ ጉባኤ አያውቁም፣ የወረዳው ቤተ ክህነት፣ ሀገረ ስብከትና ጠቅላይ ቤተክህነቱም አያውቁም
2.    እዚያ ቦታ በአጋጣሚ ሆኖ /እግዚአብሔር አያድርስና/ ችግር ቢፈጠር፡፡ ጠቅላይ ቤተክህነቱም ሀገረ ስብከቱን መጠየቁ አይቀርም ሀገረ ስብከቱም የደብሩን ተጠሪ መጠየቁ አይቀርም፡፡ ስለዚህ እንደኃላፊነት ሀገረ ስብከቱ እያወቀው መሆን አለበት፡፡ ምዕመናንም ምን አልባት የስሕተት ትምህርት እየተላለፈ እንደሆነ፣ ቃለ ዐዋዲውም እየተከበረ እንደሆነ፣ አበው ያቆዩት ሥርዓት እየተጠበቀ እንደሆነ ሊከታተሉ ሊያውቁ ይገባል፡፡

ስለዚህ በአጠቃላይ ችግሮቹ የተፈጠሩት በመጀመሪያ ያለ እድሜያቸው በሰንበት ትምህርት ቤት ውስጥ ተካተው ድርሻቸውን ሳያውቁ የሚኖሩ ስላሉ፣ ቀጥሎም በተናጠልም ሆነ በቡድን ተሰባስበው እኛ መስበክ አለብን ወይም እገሌ ካልሰበከ አይሆንም በማለት እንደግል አመለካከት በመያዝ የሚንቀሳቀሱ ስላሉ ነው፡፡ ይሄንን ደግሞ ሰበካ ጉባኤው ባለው ሥልጣን ማስተካከል ይችላል፡፡

•    በአለመግባባቱ ውስጥ ሁለት ዋና ቡድኖች እንደተፈጠሩ ይነገራል፤ የቅዱስ ገብርኤል ወርሃዊ በዓል ማግስትም ግጭቶች እንደተፈጠሩ ይታወቃል፡፡ እነዚህ ቡድኖች ምንድን ነው አካሄዳቸው? ወይም ምክንያታቸው?

ሰዎች በራሳቸው እይታ ሁለት ቡድን አለ ሊሉ ይችላሉ፡፡ እንደ ሀገረ ስብከት ግን እኛ ሁለት ቡድን አለ የምንለው ነገር የለም፡፡ በመሠረቱ ቤተክርስቲያን ዓላማዋ ሰውና እግዚአብሔርን ማገናኘት ነው፡፡ በዚህ ሕይወት ደግሞ ወንጌልን፣ ፍቅርን ትህትናን እርስ በእርስ መከባበርን መተሳሰብን እንዲይዙ ማድረግ ነው፡፡ እንደ ጌታችን መድኅኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትምህርትም የቡድን አካሄድ የመከፋፈል አካሄድ፣ የመለያየት አካሄድ አነ ዘአጵሎስ ወአነ ዘኬፋ የሚለው አነጋገር በቅዱስ ወንጌልም የተደገፈ አይደለም፡፡ እኛ ከመጣን ጀምሮ የምናየው ቅድም እንዳልኩት ነው፡፡ ከችግሮቹ ምንጮች እንደገለጽኩት ከሰንበት ትምህርት ቤት የተውጣጡ የተወሰኑ የእድሜ ገደብ ያለፋባቸውና እኛ ብቻ ነን መስበክ ማስተማር ያለብን የሚሉና ወጣቶችንም ወደ ስሜት ወደ መገፋፋት የሚያመጡና፣ የቤተክርስቲያኗ ደንብ ሥርዓትና መመሪያ ያለመቀበል ሁኔታ የሚያሳዩና እንደ ራሳቸው ሃሳብ የመሄድ ጉዳይ ይታያል በሌላ በኩል መላው ምዕመናን ማለት ይቻላል፤ ሕጉ ሥርዓቱ የሲኖዶሱ መመሪያ ተከብሮ ቤተክርስቲያን ሥራዋን በአግባቡ ታከናውን የሚል ብቻ ነው ያለው፡፡ እንግዲህ አሁን የመለያየትና የቡድን ስሜት የለውም፡፡ ሕጉና መመሪያው ሲነገር ሁሉም ይሰማል፣ ሁሉም ያከብራል እዚህ ቅዱስ ገብርኤል ሰንበት ትምህርት ቤት ያሉ ጥቂት ወጣቶች ግን የልጅነትም ሊሆን ይችላል ከረር የማለትና መድረኩን እኛ ካልያዝነው፣ ስብከቱንም እኛ ካልሰበክነው የሚል የግል አካሄድ ያሳያሉ እንጂ ከሁለት የተከፈለ ቡድን የለም፡፡

የአገር ሽማግሌዎችን አባቶች፣ እባካችሁ ይሄንን መመሪያ እንዲያከብሩ አድርጓቸው፣ ትንሽ እኛን አልሰማ አሉ የሚቻለውን ነግረናል ብለን ስናስረዳ፤ እግዚአብሔር ይስጣችሁ፥ ሸክሙን እንድናግዛችሁ ወደ እኛ ማምጣታችሁ ጥሩ ነው ብለው ብዙ ደክመዋል በዚህ ጉዳይ፡፡ የተቀበሉ አሉ፥ ልክ ነው ያሉ አሉ፡፡ አንዳንዶቹ ግን የለም አይሆንም ያሉ አሉ፡፡ እንደዚህ እንደዚህ አይነት አካሄዶች ናቸው እንጂ እንደ ሰው አባባል ሁለት ቡድን የለም፡፡

•    በቤተ ክርስቲያን ታሪክ እንደዚህ አይነት አለመግባባቶች ምንጫቸው ምንድን ነው? እንዲያው ዝም ብሎ ቃለ ዐዋዲን ብቻ ባለ ማክበር የሚፈጠሩ ናቸው ብለው ያስባሉ?

ሰው ምን ጊዜም ችግር የሚገጥመው ከሕግ፣ ከሥርዓትና ከመመሪያ ሲወጣ መሆኑ ግለፅ ነው። ያለን ቆይታ አጭር በመሆኑ እስከ አሁን ያየነው ሁኔታ ከላይ የገለፅኩትን ነው የሚመስለው። ከበስተኋላው ምንድን ነው ይሄ ነገር? ምንስ አይነት እንቅስቄሴ አለው? ወይስ የተለየ ዓላማ አለው? ወይስ ሕጉን ያለማወቅ ብቻ ነው? ወይስ ደግሞ ቃለ ዐዋዲውን ያለመቀበል ነው? እስከ አሁን እንደምናየው መመሪያው እየተነገረ እያዩ እየሰሙ ያለመቀበል ነው ያለው? ግን ከበስተኋላ ምን አለው? ተጨማሪ ነገር አለው ወይ? የሚለው ግን ትንሽ ጥናት ይፈልጋል፡፡ ሲነገራቸው ተስተካክለው በመስመር መጓዝ የጀመሩና የሄዱ አሉ፡፡ ሌሎች ደግሞ የለም እንዲህ ነው እያሉ ክርር የሚሉ አሉ፡፡ ሰው ሕሊናው እያየ አእምሮው ያስባል፡፡ ማንኛውም በአርአያ እግዚአብሔር የተፈጠረ ሰው ሲነገረው ይሰማል፤ ሲያይ ያነባል፥ ግን አንብቦ፣ ተነግሮት ሰምቶ፣ ተረድቶ፣ እውነቱን አውቆ ግን ይሄ ነው ማለት መቻል አለበት፡፡ ይሄንን ካልቻለ ችግሩ ምን እንደሆነ የሰውየው ሁኔታ ነው አላማውን የሚያውቀው፡፡

የቅዱስ ገብርኤል ሰንበት ትምህርት ቤት የራሱ የሆነ መምህር የለውም፡፡ ከዚህም የተነሳ ከብፁዕ የሀገረ ስብከቱ ሊቀጳጳስ ጋር ጉዳዩን በመመካከርና በመነጋገር፣ እንደብፁዕነታቸውም መመሪያ በመቀበል አሁን የሰበካ ጉባኤ ምርጫ ከተካሄደ በኋላ በሂደት ሰንበት ትምህርት ቤቱ በአግባቡ መምህር እንዲኖረው፣ ልጆች ተኮትኩተው የቤተክርስቲያኒቱን ሥርዓትና ደንብ ጠንቅቀው አውቀው እየተገበሩ እንዲያድጉ ለማድረግ፣ ይሄ በእቅድ ደረጃ ተይዟል፡፡ ትምህርትም ሲሰጥ እንደ እድሜ ደረጃቸው ነው። ወጣቶች አሉ፣ ህፃናት አሉ፣ አዋቂዎች አሉ፣ እንደወንጌሉም ግልገሎች፤ ጠቦቶች በጎች፣ ብሎ ይለየዋልና። እዚያ ሰንበት ትምህርት ቤት ደግሞ ተቀላቅለው ነው የሚማሩት ይህ ችግር ይፈጥራል፡፡

የትምህርት አሰጣጡ ይስተካከል ሲባል ደግሞ በአንዳንድ ሰዎች ይሄ የተለመደ ነው ይላሉ፡፡ ግን ልማድ ሲጋነን ባሕል ይሆናል ይባላልና ልማድን ትተው ሊስተካከሉና መስመር ይዘው ሊጓዙ ቃለ ዐዋዲውንም ሊያከብሩ ይገባል ማለት ነው፡፡

ሌላው ቤተክርስቲያኒቱ ውስጥ ምንም አይነት የሥራ ድርሻ የሌላቸው ያልተቀጠሩ፣ የሥራ ውል የሌላቸው ወይ ዲያቆን፣ ቄስ፣ መነኩሴ፣ መሪጌታ፣ አወዳሽ ቀዳሽ ያልሆኑ፣ እንደ አንድ ምዕመን ጸልየው ወይም ትምህርት ሰምተው መሄድ ብቻ የሚገባቸው ሆነው ሳለ በማይገባቸው አንዳንድ አስተዳደራዊ ጉዳዮች ውስጥ ጣለቃ የመግባት ነገር ይታያል፡፡ በሰንበት ትምህርት ቤትም፣ በስብከተ ወንጌልም፣ በአውደ ምህረትም ጣልቃ የሚገቡ ሰዎች ናቸው ነገሩንም እንዲባባስ እያደረጉት የሚገኙት፡፡

•    የቅዱስ ገብርኤል ገዳም አስተዳደርና ሰበካ ጉባኤ ችግሮቹን ለመፍታት ከእናንተ ጋር ያላቸው ተግባቦት ምን ይመስላል?
 

በእርግጥ አሁን ያለው ሰበካ ጉባኤ እኛ ከመምጣታችን በፊት ጊዜያዊ ተብሎ የተመረጠ ነው፡፡ በዚህ የተነሣ ብዙ ጊዜ፥ አንዳንድ ሥራዎችን ለመሥራት ሲቸገሩ እናያለን፡፡ ጠርተን በጋራ አወያይተናል፥ ተመካክረናል ጊዜያዊ ሆነው እንዴት እንደተመረጡ ለእኛም ግለፅ አይደለም፤ ምክንያቱም ባልነበርንበት ጊዜ ስለነበር፤ አንዳንድ ምዕመናንም አልመረጥንም፤ ጊዜያዊ ናቸው፤ የማለት ያለመተባበር ችግር ይታያል፡፡

እኛ ከመጣን ግን የገዳሙን አስተዳዳሪና ሰበካ ጉባኤውንም በጋራ ቁጭ አድርገን አወያይተናል፥ ማደሪያ ጉዳዩንም አገላብጠን ተመልክተን ጊዜአዊ ሰበካ ጉባኤ መሆናቸውን እነርሱም አውቀውት፥ እነርሱም ባሉበት ሆነው፣ ከወጣቱም፣ ከአገር ሽማግሌዎችም፣ ከልማት ኮሚቴም፣ ከሚመለከታቸው አካላት የተወሰኑ ይዘን የመንግሥት አካላትም በታዛቢነት እንዲገኙልን አድርገን የቃለ ዐዋዲውን ሕግና መመሪያ በጠበቀ መልኩ ተገቢውን ቅስቀሳና ትምህርት ተሰጥቶ የቤተክርስቲያኒቱን አስተዳደራዊ ሥራ በአግባቡ ሊመራና ግቢውን ሊያስከብር ሊጠብቅ የሚችል ሰበካ ጉባኤ ምርጫ እንዲካሄድ የሚል ውሳኔም ስምምነት አድርገናል፡፡
 
አሁንም ቅድመ ሁኔታዎችን በማመቻቸት ላይ እንገኛለን፡፡ እስከዚያው ድረስ ግን አሁን ያለው ሰበካ ጉባኤ ያለውን ኃላፊነት እንዲወጣና ለአንድ ቀንም ቢሆን ኃላፊነት ስላለው ግቢውን እንዲያስከብር፣ እንዲጠብቅ በተደጋጋሚ ጊዜ ተወያይተናል መመሪያ ተሰጥቷል ብፁዕ አባታችንም በሰፊው ደክመውበታል፡፡ ተፈፃሚነቱ ግን እምብዛም አይታይም፡፡ የአቅም ማደስም፣ ኃላፊነትን በአግባቡ አለመወጣት ሊሆን ይችላል እንግዲህ ምክንያቱ፡፡

በግቢው ያለው ማንኛውም እንቅስቃሴ ሰበካ ጉባኤውንም አስተዳዳሪውን በመጀመሪያ ደረጃ ይመለከታል፡፡ ስለዚህ አዛው አጥቢያው ላይ እንደ ቃለ ዐዋዲው የማስኬድ ፣ መመሪያውን የመጠበቅና የማስጠበቅ፣ መስመሮችን እንዳይለቁ የመከታተልና ቁርጥ ያለ ውሳኔና ፍትሕ የመስጠት አስተዳደራዊ ሥራ ቢሠራ ምንም አይነት ችግር አይኖርም፡፡

                                                                                    ይቆየን

ከ7500 በላይ አልባሳት ተሰበሰበ

በፈትለወርቅ ደስታ
«ሁለት ልብሶች ያሉት…..» በሚል መሪ ቃል የተጀመረው የአልባሳት ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር የቀጠለ ሲሆን የመጀመሪያውን ቀን ጨምሮ እስከ እሁድ ጥር 29 ቀን 2003 ዓ.ም ድረስ ባሉት ቀናት ከ7500 በላይ አልባሳት፣ ከ10 በላይ ጣቃ የተለያዩ ብትን ጨርቆችና ለመነኮሳት የሚሆኑ አልባሳት እንደተሰበሰበ ታውቋል፡፡

በዚህ መርሐ ግብር አልባሳቱ ከአዲስ አበባ፣ ከአዲስ ዓለምና ከኳታር እንደተሰበሰቡ ለማወቅ ተችሏል፡፡ በአልባሳት መደገፍ ያልቻሉ በርካታ ምዕመናንም መርሐ ግብሩን በገንዘብ በመደገፍ ተሳትፎ እያደረጉ ነው፡፡

አንዳንድ ምዕመናን ይዘውት ከመጡት አልባሳት በተጨማሪ ደርበው የመጡትን ጃኬትና ሸሚዝ እስከመስጠት ደርሰዋል፡፡ «ዓላማው በጣም ደስ ብሎኛል በረከትና ረድኤት አገኝበታለሁ ብዬ ነው የማደርገው፤ እኛ ለእኛ እንበቃ ነበር ነገር ግን ሁላችንም አነሳሽና መሪ እንፈለጋለን» በማለት ስሙን መግለጽ ያልፈለገ ወጣት ገልጾልናል፡፡

 

ከአገር ውስጥና ከአገር ውጭ ያሉ ምዕመናን መርሐ ግብሩ የሚከናወንባቸው ቀናት አጭር በመሆኑ መሳተፍ አለመቻላቸውን በስልክና በኢሜይል በመግለጻቸው እስከ የካቲት 6 ቀን 2003 ዓ.ም እንደተራዘመ አስተባባሪ ክፍሉ አሳውቋል፡፡

በእስከ አሁኑ መርሐ ግብር ከ800 በላይ የሆኑ ምዕመናን ተሣትፈዋል፡፡ መርሐ ግብሩ ዘወትር ከጠዋት 2፡30 እስከ ምሽቱ 2፡30 ድረስ ይካሄዳል፡፡

በአልባሳት ማሰባሰቢያ መርሃግብሩ የመጀመሪያ ቀን ከ175ዐ በላይ አልባሳት ተሰበሰበ

                                                                   በፈትለወርቅ ደስታ
 
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን «ሁለት ልብሶች ያሉት….» በሚል ስያሜ የሚከናወነው የአልባሳት ማሰባሰቢያ መርሃ ግብር በይፋ ተከፈተ በመጀመሪያው ዕለትም ከ175ዐ በላይ አልባሳት  ተሰብስቧል፡፡

ካህናት አባቶች የማኅበሩ አባላትና ምዕመናን በተገኙበት መርሃግብር በጸሎት የከፈቱት ቀሲስ ዶ/ር ሰሙ ሙሉጌታ «ሁለት ልብሶች ያሉት አንዱን ለሌላው ይስጥ» በሉቃስ ወንጌል ምዕራፍ 3÷11 » ላይ ያለውን የወንጌል ቃል መነሻ በማድረግ ትምህርተ ወንጌል ሰጥተዋል፡፡

በመቀጠልም በማኅበሩ አባላት የመዝሙር ክፍልና በአባላት ህፃናት ልጆች መዝሙር ቀርቦ የቅዱሳን መካናት ልማትና ማህበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የቦርድ ሰብሳቢ በሆኑት በወ/ሮ ዓለምፀሀይ መሠረት ስለመርሃግብሩ ዓላማና አስፈላጊነት ገለፃ ተደርጓል፡፡

በጉባዔው ላይ የተሳተፉት ምዕመናን ስለ ጉባዔው ያላቸውን አስተያየት ሲገልፁ «እግዚአብሔር ፍጥረቱን ተጠቅሞ ማንኛውንም ሥራ ይሠራል ማህበሩም በዚህ ዘርፍ ብዙ እየሠራ ነው፡፡» በየገዳማቱ ያሉትንም እንዲህ ማሰቡ በጣም ጥሩና ይበል የሚያሰኝ ነው አሁን ያየሁት እነሱ በልብስ ተራቁተዋል እኛ ግን በመንፈስ ተራቁተናል ጅምሩ ጥሩ ነው በዚሁ ይቀጥል፤ ዓላማው ያስማማናል ተጠናክሮ መቀጠል አለበት» ብለዋል፡፡
በመጨረሻም በማኅበሩ ሰብሳቢ በቀሲሲ ዶ/ር ሙሉጌታ ስዮም የመዝጊያ ንግግርና በመርሃግብሩ ለሚሳተፉ ምዕመናን ምሥጋና አቅርበሙ በጸሎት ተዘግቷል ጠዋት የጀመረው የአልባሳት ማሰባሰብ መርሃግብር ቀጥሎ በዕለቱ ከምዕመናን ከ1750 በላይ የወንዶች፣ የሴቶችና የህፃናት አልባሳት ለመሰብሰብ ተችሏል፡፡

                               
ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ለመነኮሳትና አብነት ተማሪዎች የአልባሳት ማሰባሰቢያ መርሐግብር ተዘጋጀ።

በፈትለወርቅ ደስታ
«ሁለት ልብሶች ያሉት….» በሚል ርዕስ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን ልዩ የአልባሳት ማሰባሰቢያ መርሃ ግብር ተዘጋጀ
 
የዚህ መርሃ ግብር አዘጋጅ በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳን መካናት ልማትና ማህበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ሲሆን ጥር 22/2003 ዓ.ም በማኅበሩ ጽ/ቤት በይፋ ይከፈታል፡፡ የቅዱሳን መካናት ልማትና ማህበራዊ ዋና ክፍል የቅስቀሳ አስተባባሪ ዲያቆን ደረጀ ግርማ ለማኅበረ ቅዱሳን የሬድዮ ክፍል እንደገለፁት «የመርሃ ግብሩ ዓላማ ብዙዎቹ ገዳማውያን መነኮሳትና የአብነት ትምህርት ቤት ተማሪዎች የሚለብሱትን እራፊ ጨርቅ ምግባቸውን ያሰጡበታል፤ ያንኑ ምግብ ምግብ እየሸተተ መልሰው ይለብሱና ለአገልግሎት ወደ ቤተክርስቲያን ይገባሉ፡፡ ይሄንን ማስቀረት ይኖርብናል፡፡ ሌላው ጌታችን መድኃኂታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በማቴዎስ ወንጌል በምዕራፍ 25 ላይ እንደገለጸው፥ «ታርዤ አላለበሳችሁኝም» ከሚለው ወቀሳ ለመዳንና «ታርዤ አልብሳችሁኛልና» የሚለውን ትእዛዝም ለመፈጸም ነው፡፡ በተጨማሪም በአገራችን በአልባሳት የመደጋገፍ ባሕል የለም። ይህ ባሕል ሆኖ እንዲቀጥል ቢያንስ በየሁለት ዓመት አንድ ጊዜ እንዲህ ዓይነት መርሃ ግብር ያስፈልጋል» በማለት ገልጸዋል፡፡

አክለውም «ይህ መርሃ ግብር ቢያንስ ለሁለት ዓመት ያህል የአልባሳት ችግራቸው እንዲቀረፍ በ25 ገዳማትና አድባራት ያሉ 75ዐ መነኮሳትና በ5ዐ ታላላቅ የአብነት ትምህርት ቤቶች የሚገኙ 35ዐዐ መምህራንና ተማሪዎችን በጊዜያዊነት የሚያግዝ ይሆናል፡፡»

በጊዜው የሚሰበሰቡ የአልባሳት አይነቶች ለአብነት ትምህርት ቤቶች ሸሚዝ፣ ሱሪ፣ ኮት፣ ጃኬት፣ ጫማ፣ አንሶላ፣ ጋቢ፣ ብርድልብሶች ካኔተራና የመሳሰሉትን የሚያጠቃልል ሲሆን ለመነኮሳት ደግሞ አቡጀዲ፣ ልብስ፣ ሹራብ፣ ነጠላ እና ለመነኮሳት የሚሆን ሻርፕ፣ ብትን ጨርቅ የመሳሰሉትን ያጠቃልላል፡፡

በዝግጅቱ ላይም ከ5ዐዐዐ በላይ ምዕመናን እንደሚሳተፉበት ይገመታል ያሉት አስተባባሪው የአልባሳት ድጋፍ ማድረግ ያልቻሉ ምዕመናን የገንዘብ ድጋፍ ማድረግ እንደሚችሉ ተናግረዋል፡፡

«እርስዎ የለበሱት ሌላውን ያለብሳልና» ሁሉም ምዕመን ከዚህ መርሐግብር ለመሳተፍ ወደኋላ እንዳይል አዘጋጅ ክፍሉ ያሳስባል፡፡

የአልባሳት ማሰባሰቢያ መርሃግብር የማኅበረ ቅዱሳንን ሕንፃ ጨምሮ በ15 የሰንበት ትምህርት ቤቶች ይከናወናል፡፡ 

gonder4.jpg

የጥምቀት በዓል ፋይዳና ተግዳሮቶቹ

በዶ/ር ቤተልሔም ግርማ
 
gonder4.jpgበስምንት ዓመት የጎንደር ቆይታዬ በየዓመቱ በዓሉን የመካፈል ዕድል አግኝቻለሁ። እያንዳንዱ ዓመት የየራሱ የሆነ ለየት ያሉ ትዕይንቶች ነበሩት። በአጠቃላይ ግን የታዳሚው ቁጥር ለማመን በሚያስቸግር መልኩ ከዓመት ወደ ዓመት እየጨመረ መጥቷል። በሌላ መልኩ ደግሞ ወጣቱ በበዓሉ ላይ ያለው  ተሳትፎ ለውጥም ከቤተ ክርስቲያን ሥርዓት አንፃር በጣም የሚበረታታ ነው።

 
የጥምቀት በዓል ከጊዜ ወደ ጊዜ የዓለም አቀፉን ኅብረተሰብ ቀልብ እየሳበ የመጣ ታላቅ ሃይማኖታዊ ክብረ በዓል ነው። ሀገራችን ኢትዮጵያ የጌታችን የመድኀኒታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ጥምቀት ከሚያከብሩ ጥቂት የዓለማችን ሀገሮች አንዷ እና ዋነኛዋ ናት። ይህ ታላቅ ሃይማኖታዊ በዓል ከሕዝቡ ባህል ጋር ጥብቅ ትስስር ያለው ስለሆነም ከሃይማኖታዊ በዓልነቱ ባሻገር ባሕላዊ ፋይዳውም ጎን ለጎን የሚሄድ ነው። የዚህም ቋሚ ምስክር ከዚህ በዓል ጋር የሚነሱ እና የሚወሱ የሥነ-ቃል ሀብቶች ናቸው።

ለሦስት ቀናት ያህል (ከከተራ እስከ ቃና ዘገሊላ) በተከታታይ የሚከበረው ይህ ታላቅ ሃይማኖታዊ ሥርዓት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መገለጫ ከመሆኑም በላይ ለምዕመኑ በረከት የሚያስገኝ ነው።

«እልልታን የሚያውቅ ሕዝብ ምስጉን ነው» መዝ 88፥15

desie.jpgታቦታቱ ከየአብያተ ክርስቲያናቱ በክብር ወጥተው በሕዝቡ እልልታ፣ ሽብሽባ እና በካህናቱ ውብ ያሬዳዊ ዜማ ወደ ወንዝ ወይም የተዘጋጀ የውኃ ቦታ በመውረድ የሚጀምረው ይህ በዓል ሕዝቡን በሰፊው የሚያሳተፍ ነው።

ይህንን ውብና ድንቅ ክብረ በዓል ለማክበር አገር ተሻግረው ሥርዓቱን ለማየት የሚመጡ የውጭ ሀገር ዜጎች ከዓመት ወደ ዓመት ቁጥራቸው እየጨመረ መጥቷል። ይህም ጥንታዊት፣ ኦርቶዶክሳዊትንና ሐዋርያዊት የሆነችውን የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያናንን በዓለም አቀፍ ደረጃ ለማስተዋወቅ ያለው ድርሻ በዓለም ከፍተኛ መሆኑ አያጠራጥርም። በማያውቁት ሀገር እና በማያውቁት ቋንቋ በሚደረገው መጽሐፍ ቅዱሳዊና ሰማያዊ ሥነ- ሥርዓት መንፈሳዊ ሀይል ተማርከው የሚጠመቁም የውጭ ዜጎች አልጠፉም።

ጥምቀት በጎንደር

በዓሉ በድምቀት ከሚከበርባቸው ከተሞች አንዷ ጎንደር ናት። የብዙ ታቦታት ሀገር የሆነችው ይህች ከተማ በዓይነቱ ለየት ያለ ባሕረ ጥምቀትም አላት። ይህ የአፄ ፋሲል መዋኛ የነበረው ታሪካዊ ባሕረ ጥምቀት ለጥምቀት በዓሉ ትልቅ ግርማ ሞገስ የሚሰጥ ነው።

የዚህች ጥንታዊት ቤተ ክርስቲያን የነገ ተስፋ እና የቅርሱና የሥርዓቱ ውርስ ተቀባይ የሆነው ወጣት gonder5.jpgበበዓሉ ላይ ትልቅ ተሳትፎ ያደርጋል። በዓሉ ከመከበሩ ከወራት በፊት በየሰንበት ትምህርት ቤቱ በልዩ ኮሚቴዎች የተለያዩ እንቅስቃሴዎች ሲያደርግ ቆይቷል።

በተለይ ደግሞ በዓሉ ጥቂት ቀናት ሲቀሩት አካባቢን ከማስዋብ ጀምሮ በከተማዋ ለሚገቡ እንግዶች ኢትዮጵያዊ የሆነ አቀባበልና መስተንግዶም ተደርጓል።

ከጥቂት ዓመታት ወዲህ ታይቶ እና ተሰምቶ በማይታወቅ መልኩ ለታቦታቱ ልዩ ክብር በመስጠትም የምንጣፍ ማንጠፍ ሥነ ሥርዓትንም ጀምረዋል። ይህ አባቶችን ከማስደመም አልፎ በወጣቱ ሥነ ሥርአትም ያላቸውን እምነትም ጨምሯል። ወጣቱ ለሃይማኖቱ ያለውን ፍቅርና ተቆርቋሪነትም በግልጽ አሳይቷል።

ከዚህ ባለፈም ወጣቱ የበዓሉ ዝማሬ በመንፈሳዊ ሥነ ሥርዓት እንዲከናወን ሥርዓት አልባ የሆኑና ሃይማኖታዊ መሠረት የሌላቸውን ጭፈራና ሆይታም ለማስቀረት ትልቅ እና አመርቂ የሆነ አንቅስቃሴ አድርጓል።

የዘንድሮም የጥምቀት በዓል ከመቼውም ጊዜ በላይ በደማቅ መልኩ ተከብሮ አልፏል። ከላይ በጽሑፌ ለመግለጽ እንደሞከርኩት እያንዳንዱ ዓመት የየራሱ መገለጫዎች እንዳሉት ሁሉ በዘንድሮውም አንዳንድ ለየት ያሉ ክስተቶች መታየታቸው አልቀረም።

ወደ መቶ ሺህ ገደማ የውጭ ሀገር ዜጎች፣ በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያንና መንፈሳዊ ተጓዦች የታደሙበት የዘንድሮው የጥምቀት በዓል በሕዝቡ ቁጥር ረገድ ከቀድሞው ዓመታት ሁሉ የላቀ ነበር። ይህንን በቁጥር የበዛ ሰው ለማስተናገድም ሲባል በባሕረ ጥምቀቱ ቅጥር ግቢ ውስጥ ልዩ የሆነ የመቀመጫ ቦታ ተሰናድቶ ነበር ። ይህ በእግር ኳስ ሜዳ ውስጥ እንዳለ ክቡር ትሪቢውን ያለ የመቀመጫ ሥፍራ በአፄ ፋሲል መዋኛ ገንዳ ዙሪያ የተገነባ ነው። በዚህም ልዩ የሆነ ቦታ እንግዶች በክብር ሲስተናገዱ ውለዋል።

ያለ ምዕመናን?

የኢትዮጵያ ምዕመን በእንግዳ ተቀባይነቱ የታወቀ በመሆኑም ሥነ ሥርዓቱን ለመመልከት ለመጡት የውጭ ዜጎች የተለመደውን አቀባበል አድርጓል። የክብረ በዓሉ አፈጻጸም ሳያጠራጥረው ያላለፈ ግን ጥቂት አይባልም። ሕዝበ ክርስቲያኑ ሃይማኖታዊ ሥርዓቱን በቅርብ ለመከታተል የሌሊቱ ጨለማና ብርድ ሳይበግረው፥ ጣፋጭ እንቅልፉ እና ሙቅ መኝታው ሳያታልለው፥ በቦታው ቢገኝም እንኳን በቅርበት ለማየት ቀርቶ በአካባቢው የሥነ ሥርዓት አስከባሪ ወደ ኋላ እንዲመለስ ተደርጓል።

ምንም እንኳን የሀገር ጎብኚዎቹ(ቱሪስቶች) ለማየት የሚመጡት ባሕረ ጥምቀቱን ካህናቱንና ሃይማኖታዊ ሥርዓቱን ቢሆንም ለዚህ ሁሉ ውበት የሚሰጠው ምዕመኑ ጭምር ነውና ምዕመኑም እንድ መስህብ መሆኑ መዘንጋት የለበትም። ስለዚህም ቢያንስ የተወሰነው ሰው ቀረብ ብሎ እንዲያይ(እንዲታደም) ቢደረግና የሕዝቡንም ጉጉት ለማስተናገድ ቢሞከር የተሻለ ይሆን ነበር። ብዙሃኑ ወጣት ለበዓሉ ዝግጅት እስፓልት ማጠብ እንኳን ሳይቀረው ደክሞ የበይ ተመልካች መሆኑ ቅር ማሰኘቱ አልቀረም። የሕዝቡ ቁጥር እንዳለ ሆኖ እንግዶች ቦታ ቦታ ከያዙ በኋላ እንኳን ምዕመኑ የሚገባው ክብር ተሠጥቶት ቢስተናገድ ተገቢ ነበር።

የአውሮፓውያን መንፈሳዊያን በዓላት ዓለማዊነት

በአየርላንዳውያን ዘንድ መጋቢት 17 (እ.ኤ.አ) የሚከበር ሃይማኖታዊ በዓል አላቸው። በዓሉ ፓትሪክስ የሚባል ከ387-461 ዓ.ም እንደኖረ የሚታመንና በአየርላንድ (በቀድሞዋ ሮማ) ታዋቂ የሆነ መንፈሳዊ አባታቸው ነው።

17ኛው ክፍለ ዘመን መጀመሪያ መከበር የጀመረው ይህ ክብረ በዓል፥ የሮም ቤተ ክርስቲያን ንጹሕ ሃይማኖታዊ ክብረ በዓል ነበር። ቀስ በቀስ ግን የአየርላንድን ባሕል ብቻ የሚያሳይ ዓለማዊ ክብረ በዓል እየሆነ መጥቷል።

patrics1.jpgpatrics2.jpg

 
 
 
 
 
በ1990ዎቹ መካከል የአየርላንድ መንግሥት ይህን በዓልን የአገሪቱን ገጽታ ለመገንባትና ባሕሏን ለማሳየት እንቅስቃሴ አድርጎ ተጠቅሞበታል።

የአየርላንድ የሃይማኖት መሪዎች በዓሉ ዓለማዊ ገጽታ እየተላበሰ መሄዱን ይገልጻሉ። በ2007 ዓ.ም (እ.ኤ.አ) ፋዘር ቪንሰንት የተባሉ አየርላንዳዊ ቄስ the world’s magazine በተባለ መጽሔት ላይ ባወጡት ጽሑፍ «በዓሉ የቤተ ክርስቲያን ሃይማኖታዊ ክብረ በዓል፤ ዓላማውም ሃይማኖታዊ መሆኑን ማስገንዘቢያ ጊዜው አሁን ነው» ይላሉ።

patrics.jpgበያዝነው የፈረንጆች አመት መጋቢት ወር ላይም በፋሽን፣ በፈንጠዝያ፣ በሙዚቃ፣ በመንገድ ላይ ቲአትሮችና በካርኒቫል ለማክበር እቅድ ተይዟል። 

በሌላ ሁኔታ የ”Assumption Day” ከዚሁ ዕጣ ፈንታ አላለፈም። Assumption Day በሀገራችን ፍልሰታ ብለን የምናከብረው የእመቤታችን ትንሣኤና ዕርገት በዓል ነው። ዛሬ ዛሬ በስዊዘርላንድና በብዙ የአውሮፓ ሀገሮች ምንም ዓይነት የሚታይ መንፈሳዊ እንቅስቃሴ ሳይኖር በርችት፣ በችቦ፣ ጭፈራ፣ በህብረ ቀለማትና በመንገድ ላይ ትርዒት ብቻ የሚከበር ሆኗል።

እነዚህ በዓላት መንፈሳዊነታቸው የደበዘዘውና ሲብስም የጠፋው የምዕራባዊያን አብያተ ክርስቲያናት እንደ ቤተ ክርስቲያን መቆም ሲያቅታቸውና ተልዕኳቸው እየተዳከመ ሲሔድ መሆኑ አይረሳም። በኢትዮጵያ ግን ቤተ ክርስቲያን አገልግሎቷ ሳይገታ በዓሉን በመንፈሳዊ ይዘቱ የሚያክብረው ምዕመን ሳይጠፋ ማቀላቀሉ ይጠቅም ይሆን? በጥብቅ ማሰብ ያሻል!

የበዓሉ ተግዳሮት


ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተለወጠ የመጣው የጥምቀት አከባበር ሌላ ትልቅ የማንነት ጥያቄም ከፊቱ ተጋርጦበት ይገኛል። ፈረንጆቹ እንዲህ አይነት የሕዝብ ስብስብ እና ሥርዓት በሃገራቸው የተለመደ ባለመሆኑ ይሄንን ክብረ በዓል ወደ ሚያውቋቸው የአደባባይ ትሪዒቶች ማጠጋጋታቸው አይቀርም። ከዚህም አንዱና ዋነኛው “ካርኒቫል” ነው። ይህ በተለይ በላቲን አሜሪካ አካባቢ የሚታወቅ የአደባባይ ትርዒት ነው። በዚህ ወቅት ብዛት ያላቸው ሰዎች ቀለም የበዛበት ወይም ለየት ያሉ አልባሳትን በመልበስ በየአደባባዩ ሲጨፍሩና ሲዝናኑ ይከርማሉ። ይህ ፍጹም አለማዊ የሆነ የአደባባይ ትርዒት ከየትኛውም መንፈሳዊ ክብረ ባህል ጋር ማወዳደር ከመቀሰፍ አያድንም።

የዘንድሮውን የጎንደር የጥምቀት በዓል ካርኒቫል እንዲኖረው አንዳንድ እንቅስቃሴዎች ተደርገዋል። ከዚህም ውስጥ ዋነኛው በየመንገዱ ላይ ጊዜአዊ ድንኳኖችና ዳሶችን በመጣል የባህላዊ መጠጥና ምግቦች መስተንግዶ ነው። እነዚህ በዋና ዋና መንገዶችና በጥምቀተ ባህሩ አቅራቢያ የተተከሉ ዳሶች ውስጥ ምግብና መጠጥ ከመስተናገዱም ባለፈ ዓለማዊ ዘፈኖችም ይከፈታሉ። ይህ መስተንግዶ ለእንግዶች ጥሩ አቀባበል ተያያዥ ጉዳቶችንም ማምጣቱ አልቀረም። ከዚህ ባለፈ የሚያስፈራው ደግሞ ይህ አካሄድ ወደ ፊት ወደ የት ሊያመራ እንደሚችል ነው። በአህዛብና በአማሌቃያውያን ጭምር የሚከበረው የጥምቀት በዓል የሕዝብ በዓል መሆኑ እንዳለ ሆኖ ሃይማኖታዊ መሠረቱ ግን መቼም ቢሆን ለአፍታ እንኳን ሊዘነጋ አይገባውም። ማንም ከየትኛውም አይነት የአደባባይ ትርዒት ጋር ቢያመሳስለው እንኳን የበዓኡን ትክክለኛ ትርጉምና አመጣጥ ማስረዳትና ማስተዋወቅ የእኛ የእምነቱ ተከታዮች ኃላፊነት ነው።

ከቱሪዝም አንፃርም ቢሆን ከፍተኛ የሃገር ውስጥ ገቢ የሚያስገኘው ይህ ክብረ በዓል ሃይማኖታዊ ይዘቱ ተጠብቆ እንዲቆይ ሁሉም የየራሱን ኃላፊነት መወጣት ይጠበቅበታል። በዓሉም ጥንታዊነቱን ጠብቆ እንዲዘልቅ ትልቅ ጥንቃቄና ትኩረትን ይሻል።

እንግዲህ ዓለምን የሚያስደምምና የሚያማልል ሃይማኖታዊ ትውፊት ባለቤት የሆነችው ቤተ ክርስቲያን የባለቤትነት ጥቅም ትሻለች። ኢትዮጵያና ቤተ ክርስቲያንን  ቤተ ክርስቲያንንና  ኢትዮጵያን ለይቶ ማየት ይከብዳል። ኢትዮጵያን ኢትዮጵያ የምታሰኛትን ይህችን ቤተ ክርስቲያን በክብረ በዓላቱም ብቻ ሳይሆን ሁሌም ማሰብ ግድ ይላል። በአዘቦቱም ቢሆን በመላ አገሪቱ ያሉ የቱሪስት መዳረሻዎች በአንድም በሌላም መንገድ ከቤተ ክርስቲያን ጋር የተገናኙ በመሆናቸው ቤተ ክርስቲያኗን መጠበቅ ሃገራዊ ግዴታ ያደርገዋል።

የቤተ ክርስቲያን ዓላማዋ ምንድን ነው?

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከብርሃነ ትንሣኤው በኋላ ለምዕመናን የሚገለጠው በቤተ ክርስቲያን ነው። ስለዚህ ቤተ ክርስቲያን ክርስቶስን ለዓለም እንድታሣይ ታዛለች። ለዚህም ነው በዘመነ አስተርእዮ(በመገለጥ) ክርስቶስን ለመስበክ ቤተ ክርስቲያን ታቦትን ይዛ የምታወጣው። በክብረ በዓሉም የምናሳየው ደስታ ክርስቶስ በመገለጡ ምክንያት ያገኘነውን ደስታ የሚያመለክትና ይሄንን ደስታ ለዓለም ማሳየታችን ነው።

ታቦቱ ሲወጣ ሴቶች በእልልታ ወንዶች በጭብጨባ የምናሰማው ደስታ፥ እኛ ከመሠዊያው ላይ ያገኘነውን የክርስቶስ ሥጋ በልተን ደሙን ጠጥተን ደስ ብሎናል። እናንተም ከደስታው ተካፋይ ሁኑ ማለቷ ነው፣ ቤተ ክርስቲያን።

በመሠረቱ በክርስትና፥ የበዓል ድምቀት፥ የሚያከብሩት ሰዎች መንፈሳዊነት ነው። በዓሉም ደምቆ ተከበረ ማለት ምዕመናን ሥጋ ወደሙ ተቀበሉ ማለት ነው። ቤተ ክርስቲያን እንደዚህ ነው የምታምነው።  

እንደ እኔ እንደ እኔ

ከኢኮኖሚ ከቱሪዝም አንጻር ስንመለከተው የቱሪስቶችን የቆይታ ጊዜ በማራዘም ከፍ ያለ ገቢን ለማግኘት መስራት በራሱ የሚነቀፍ አይደለም። ገቢን ለማሳደግና ልማትን ለማፋጠን የሚደረገው እንቅስቃሴ ግን ለገቢው መገኘት ዋነኛ ምክንያት የሆነውን የበዓል ሥነ ሥርዓት እንዳያደበዝዘው ማሰብንም ይጠይቃል። ለምሳሌ የበዓሉ መንፈሳዊ ሥነ ሥርዓተ ከተጠናቀቀ ታዳሚው ምዕመንም ከተሰናበተ በኋላ ባሉት ተከታታይ ዕለታት ቢደረግ የተሻለ ሳይሆን አይቀርም። አንዱ ሥነ ሥርዓት ሌላውን ሳይጋርደው የአንዱ ታዳሚ ሌላውን ሳይገፋው ከሁለቱም የሚገኘውን ጥቅም ማሳደግ (maximizing the profit) ብልህነት ነው። ከምንም በላይ በዓሉን ስናስብ ቀዳሚው ባለቤት ክርስቲያኑ ነውና ክርስቲያናዊ ፍላጎቱ ባይጎድልበት ለሁሉም ይጠቅማል። በግድ በአንድ ዕለት ይሁን ከተባለ እንኳን በቦታ መለያየቱ ሌላው አማራጭ ይሆናል። በባህረ ጥምቀቱና ታቦታቱ በሚያልፉባቸው ጎዳናዎች መንፈሳዊው ሥርዓት (ዝማሬው ዕልልታው) በሌሎች ጎዳናዎችና ሜዳዎች ደግሞ የካርኒቫሉ ትርኢት ቢካሔድ ሁሉም የወደደውን ያነሣል። ማንም የወደደውን ይመርጥ ዘንድ መብቱን መስጠት የሠለጠነ አሠራር ነውና አንዱ በሌላው ላይ ሲደርብ ግን ሌላኛውን ወገን ያስከፋልና ቢታሰብበት ብንመካከርበት ይበጃል እላለሁ።
 
(ይህንን ጽሑፍ የላኩልንን ዶ/ር ቤተልሔም ግርማን በእግዚአብሔር ስም እናመሰግናለን። የማኅበረ ቅዱሳን መካነ ድሮችን ይጎብኙ፣ ለመካነ ድሮቻችን ይጻፉ።)
 
Timketal8n.jpg

የመርካቶ ሌላኛዉ መልክ

በአልታየ ገበየሁ
Timketal8n.jpg

Timketal6n.jpgመርካቶ የሚለውን ቃል እዚህ ጋር ስናነብ መቼም በየሕሊናችን የሚመጡ ብዙ የመርካቶ ሥዕሎች ይኖራሉ ፡፡ በተለይ ግርግሩ፣ ማጭበርበሩ፣ ሌብነቱ፣ በቀላሉ የማይገታዉ አመጹ፣ ምንም ነገር ፈልጎ የማይታጣበት መሆኑ፣ ቆሻሻው….በነዚህ ሁሉ ነገሮች እንደ መርካቶ ቅድሚያዉን የሚይዝ አካባቢ የሚኖር አይመስለኝም፡፡

Timketn.jpgዛሬ የመርካቶን ሌላኛውን መልክ እንይ፡፡ በመርካቶ ውስጥ የሚኖሩ ነዋሪዎች፣ ነጋዴዎች እና ወጣቶች በደንብ ከሚታወቁባቸዉ  ነገሮች መካከል አንዱ መንፈሳዊ አገልግሎታቸው ነዉ፡፡ ሁለት ወይም ሦስት ሆነው ሙሉ ቤተ ክርስቲያን የሚያሠሩ፣ ነዳያንን የሚያበሉ፣ የሚያለብሱ፣ በየዓመት በዓሉ የተቸገሩ ወገኖቻችን ከሌላው ወገናቸው ባልተናነሰ መንገድ በዓሉን እንዲያከብሩ በገንዘብ እና ለበዓላት በሚያስፈልጉ ነገሮች የሚረዱ በትክክል ገንዘባቸው ከየት እንደተገኘ የተረዱ ወገኖችን የያዘ አከባቢ መርካቶ ነው፡፡

Timketal7n.jpgመርካቶ ለሀገሪቷ ኢኮኖሚ ዋልታ አንዱ መሆኑ አይዘነጋም፡፡ ይሁን እንጂ ለቤተ ክርስቲያንም ትልቅ የገንዘብ እና የሰው ኀይል ምንጭ እንደሆነ ቤተ ክርስቲያኒቷ ምን ያህል እንደተገነዘበች እርግጠኛ አይደለሁም፡፡ በአራቱም ማዕዘን የሚገኙ የገጠር አብያተ ክርስቲያናት ሕልውና እንዳይጠፋና በነዚሁ አከባቢ ለሚኖሩ ምዕመናን ተስፋ በመሆን እያገለገሉ ያሉ የቤተ ክርስቲያን አለኝታ የሆኑ የክርስቲያን ወገኖችን የያዘ ቦታ መርካቶ ነው፡፡

የዘንድሮውን የጥምቀት በዓል ደግሞ እንዴት አድምቀው እንደሚያከብሩት ገንዘባቸውን እና ጉልበታቸውን እንዴት ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት እንደሚያውሉት ያሳዩበትን ታላቅ ሥርዓት እንይ፡፡

Timketal5n.jpgየመርካቶ መሬት ወትሮ ከሚታወቅበት ቆሻሻነት ጸድቶ  እሱም  እንደ አዲስ ክርስቲያን ተጠምቆ በቄጠማ፣ በምንጣፍ አምሮበት ለሚያይ የወትሮው መርካቶ ነው ብሎ ለማመን በጣም ያስቸግራል፡፡ አየሩ በዕጣን መዓዛ ተሞልቶ፣ በመዝሙርና ዕልልታ ደምቆ ልዩ ልዩ ቀለማት ባሏቸው ፊኛዎችና ጥቅሶች ተውቦ ለሚያየው እውነት ይህ መርካቶ ነው ብሎ እንዲጠይቅ ያደርገዋል፡፡

በየአደባባዩና በየቦታዉ ድንኳን ተጥሎ ‹‹ካልባረክ¤ኝ አልለቅህም›› የሚለው የአባታችን የያዕቆብ የእምነት ቃል ተሰቅሎበት ምዕመናን የእግዚአብሔርን በረከት የሚጠብቁበት ብዙ ማረፊያ ቦታ ያለበት የጥምቀት በዓል በመርካቶ ነው የሚገኘዉ ቢባል ማጋነን አይሆንም፡፡

ምዕመናን ጠበል ጸዲቅ አዘጋጅተው ለበዓሉ ታዳሚ ያደሉበት መስተንግዶ፣ በዓሉን የንግድ በዓል ለማድረግ የሚጥሩትን አንዳንድ ነጋዴዎችንም የተከላከሉበት ሥርዓት ማስከበር በመርካቶው የበዓል አከባበር ላይ የታየ አንዱ ውበት ነበር፡፡

Timketal4n.jpgወጣቶች በልዩ ልዩ ቲሸርቶችና ጥቅሶች ደምቀው ቄጠማ በመጎዝጎዝ፣ ርዝመቱ በውል የማይታወቀውን ምንጣፍ በመጠቅለል እና በመዘርጋት ታቦታቱን ያከበሩ ካህናት በባዶ አስፓልት ላይ እንዳይራመዱ የሚፋጠኑትን ወጣቶች ስናይ የእግዚአብሔርን ድንቅ ሥራ ሳናደንቅ አናልፍም፡፡

መቼም ከኦርቶዶክሳዊት ሃይማኖት የወጡ እና በሌላ እምነት ስር ያሉ ወጣቶች ክርስቲያን ባለመሆናቸዉ ወይም በመውጣታቸዉ የሚቆጩበት ቀን ብትኖር የዛሬዋ የጥምቀት በዓል ናት የሚል እምነት አለኝ፡፡

ለወትሮ መርካቶ ውስጥ ሌባ ሲያባርሩ፣ የተጣሉ ሲያስታርቁ፣ ተራ ሲያስከብሩ የምናያቸው ፖሊሶች እንኳን ሥራ አጥተው ለበዓሉ ሞገስ ሆነው እንደማንኛዉም ምዕመን ታዳሚ ሆነው ነበር የዋሉት፡፡ ፓሊስ መሆናቸው እንኳን የሚታወቀው በለበሱት ዩኒፎርም ነው ማለት ይቻላል፡፡

Timketal2n.jpgታዲያ ቤተ ክርስቲያን፣ የሰንበት ትምህርት ቤቶች እና ሌሎች የሚመለከታቸዉ የመንፈሳውያን ማኅበራት ይህንን ጊዜ ትልቅ የቤት ሥራ እንደሚጠብቃቸው ልብ ሊሉት ይገባል፡፡ ጌታችን ወደኔ የመጣውን ወደውጭ አላወጣውም ብሏልና እነዚህን ወጣቶች አሳልፈን እንዳንሰጥ የተቀበልነውን አደራ እናስታዉስ፡፡ ስለዚህ ቢታሰብላቸው፡፡

kidstmaryamtimket5.jpg

የጌታችን የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ጥምቀት በጃንሜዳ።

በፈትለወርቅ
 
በከተራ ዕለት
kidstmaryamtimket5.jpgየ2003 ዓ.ም የጌታችን የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ጥምቀት ዋዜማ የከተራ በዓል በታላቅ ድምቀት ተከብሯል። በዋናው በዓል ዋዜማ፥ ከሥርዓተ ቅዳሴው ፍጻሜ በኋላ ታቦታተ ሕጉ ከመንበረ ክብራቸው ተነስተው በየምዕራፉ በሊቃውንት አባቶች ስብሐተ እግዚአብሔር እየተደረሰ በሰንበት ት/ቤት አባላትና ምዕመናን መዝሙር እየተዘመረ ወደ ባሕረ ጥምቀቱ አምርተዋል።
 
የበዓሉ አከባበርም ከዓመት ዓመት ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን እየጠበቀ፣ እየደመቀና እያሸበረቀ እየሔደ እንደሆነ በግልጽ ይታያል። መንገዱ ሁሉ ጽዱ፥ በሰንደቅ ዓላማና በዓሉን በሚመለከቱ ጥቅሶች አሸብርቋል። ከታቦታቱ ፊት መስቀልና ቅዱሳት ሥዕላት ጥላናkidstmaryamtimket3.jpg መረዋሕ የያዙ ዲያቆናት፥ በሰልፍ ሆነው የሚዘምሩ ጥንግ ድርብና ካባ የለበሱ መዘምራን፥ የደንብ ልብስ የለበሱ የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች፥ ፀአዳ የለበሱ የማኅበረ ቅዱሳን መዘምራን የጌታችን ጥምቀት የሚመለከቱ መዝሙሮችን በመዘመር፥  ወጣቶች ግራና ቀኝ እጅ ለእጅ በመያያዝ ሕዝበ ክርስቲያኑን ወደ ቀኝና ወደ ግራ ከፊትና ከኋላ በማድረግ ያለ ምንም ትርምስና ግርግር የተለያዩ ጥምቀትን የሚመለከቱ መዝሙሮችን በመዘመር፣ ወጣቶችም ፊት በመቅደም ለታቦታቱ ክብር ያዘጋጁትን ምንጣፍ በማንጠፍና ቄጠማ በመጎዝጎዝ የእግዚአብሔር ማደሪያ ለሆኑት ታቦታተ ሕጉና ለአባቶቻችን ካህናት ልዩ ክብር በማሳየት ወደ ባሕረ ጥምቀት/ጃንሜዳ/  ደርሰዋል። 
 
kidstmaryamtimket10.jpg
በጃንሜዳ ባሕረ ጥምቀተ፥ ከየአቅጣጫው የሚመጡ ታቦታት የሚያድሩ ሲሆን፣ ከደቡብ መንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም፣ መንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ፣ ታዕካ ነገሥት በአታ ለማርያምና መንበረ መንግሥት ቅዱስ ገብርኤል፥ ከምሥራቅ ገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ፣ ደብረ ነጎድጓድ ቅዱስ ዮሐንስ፣ ቀጨኔ ደብረ ስላም መድኀኔዓለምና መንበረ ልዑል ቅዱስ ማርቆስ፥ ከሰሜን ገነተ ኢየሱስና አንቀጸ ምሕረት ቅዱስ ሚካኤል እንዲሁም ከምዕራብ መካነ ሕይወት ገብረ መንፈስ ቅዱስ ናቸው።
ታቦታተ ሕጉ ቦታቸውን ይዘው ከቆሙ በኋላ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ ዘኢትዮጵያ በዓሉን አስመልክተው ሲገልፁ« በዓሉ በመላው ኢትዮጵያ እንደሚከበርና በዓሉን የምናከብር ሁሉ የክርስቶስን ሥራ ሰላምን ለመስበክ እንጅ ሌላ እንዳልሆነ በማሳየትም ጭምር መሆኑን ገልፀው አክለውም ቱሪስቶች ወደዚች አገር የሚመጡት የተሻለውን ለመውሰድና ለመረዳት ተረድቶም ለመፈጸም ነው። ስለሆነም ቤተ ክርስቲያን በዓሉን ስታከብር የቱሪስትን ዐይን ለመማረክ ብላ ሳይሆን፥ የእምነትን ትክክለኛ አቋም ይዛ ነው። ይህ ደግሞ የቀደሙ አባቶች ያቆዩልን ሥርዓት የየዘመኑን ትውልድ ሁሉ ያካተተ ነው። ቱሪስቶች የሚመጡት የአገሪቱን ቱሪዝም ገቢ ለመጨመር አስበው ሳይሆን የቤተ ክርስቲያንና የምዕመናኑ ልባዊ ፍቅር ስቧቸው ነው። ስለዚህ ፍቅራችሁ የተስማማ ይሁን፥ እናንተን እያዩ የሰማዩ አባታችሁን እንዲያመሰግኑት የሚለውን ይዘን በዓሉ በሰላምና በመፈቃቀር እንዲከበር አሳስበዋል።

በዓሉን አስመልክቶ ያነጋገርናቸው ዶ/ር አባ ኀ/ማርያም በጠቅላይ ቤተ ክህነት የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልዕኮ መምሪያ ሓላፊ «የዛሬው በዓል የከተራ በዓል ነው። ከተራ ስንል በዋዜማው ምዕመናን ተሰብስበው በአንድነት የሚሆኑበት ነው። ከተራ ማለት መሰብሰብ ክብ ሰርቶ በአንድ ላይ ምስጋና ማቅረብን የሚያመለክት ቃል ነው። በአራቱም ማዕዘን ምዕመናን በአንድ ላይ ሆነው በዓሉን ያከብራሉkidstmaryamtimket6.jpg ይህም በዓል መገለጥ/epiphany/ ይባላል። በዕለቱ ደግሞ ነገ ጌታችን በተጠመቀ ጊዜ መገለጥ ሆኗል። የአብ የወልድ የመንፈስ ቅዱስ አንድነትና ሦስትነት ተገልጿል። ክርስቲያኖችም ይህንን በዓል የምናከብረው ለበረከትና ለረድኤት ነው። ምዕመኑ በተለየ ሁኔታ ሰላማዊ በሆነ መንገድ ማራኪና አስደናቂ ነገር ለቤተ ክርስቲያኒቱ እያበረከተ መሆኑንና ይህ ደግሞ የቤተ ክርስቲያኒቱንም የአገሪቱንም መልካም ገፅታ የሚያንፀባርቅ ይሆናል። አገራዊና ዓለም አቀፋዊ ገጽታውም በጣም ከፍተኛ ትኩረት የሚሰጠው መሆኑንና በዓሉ በነገው ዕለትም በከፍተኛ ድምቀት እንደሚከበር ገልጸዋል።

ከቅዱስነታቸው ጸሎተ ቡራኬ በኋላ የዕለቱ ተረኛ ደብር የታዕካ ነገሥት በአታ ለማርያም ገዳም ሊቃውንት «ሃሌ ሉያ ወረደ ወልድ…» የሚለውን ያሬዳዊ ዜማ አቅርበዋል።

በብፁዕ አቡነ ፊሊጶስ የዕለቱ መልዕክትና በዓሉን አስመልክቶ ትምህርተ ወንጌል ተሰጥቷል። በመጨረሻም ቅዱስነታችው ቃለ ቡራኬና ምዕዳን ሰጥተው ታቦታተ ህጉ ወደ ተዘጋጀላቸው ድንኳን ገብተዋል።

አገልጋዮች ካህናትና ምዕመናንም ሌሊቱን በትምህርተ ወንጌል፣ በማሕሌትና በዝማሬ አሳልፈዋል። የቅዳሴ ሥርዓቱም ከሌሊቱ 6፡00 ጀምሮ እስከ 9፡00 ሰዓት ድረስ በታዕካ ነገሥት በአታ ለማርያም ገዳም ካህናት ተከናውኗል። በዕለቱ ብዙ ምዕመናን ቅዱስ ቁርባን ተቀብለዋል።

በዓለ ጥምቀት
ቅዱስነታቸው ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ፣ የአድባራትና የገዳማት አስተዳዳሪዎች፣ መነኮሳት፣ ካህናት ልብሰ ተክህኗቸውን ለብሰው ቅዱሳት መጻሕፍትን ይዘው፥ በአራቱም ማዕዘን ከበው የጥምቀተ ባሕሩን የቡራኬ ሥርዓት ያደርሳሉ፡፡ በቅዳሴና በማሕሌት ከታቦታተ ሕጉ ጋር ያደሩት ምዕመናን እንዲሁም ከየቤታቸው በሌሊት ተነስተው የመጡት፥ ባሕረ ጥምቀቱን ከበው ቆመው ሥርዓቱን እየተከታተሉ ምሥጋና ያቀርባሉ፡፡

በቅዱስነታቸው፣ በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትና በካህናት በዕለቱ የሚደርሰው ጸሎተ አኮቴት በንባብና በዜማ ተደርሶ ባሕረ ጥምቀቱ በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ተባርኮ ምዕመናን ፀበል ተረጭተዋል፡፡

በመቀጠልም የታዕካ ነገሥት በአታ ለማርያም ገዳም ሊቃውንት መዘምራን ዕለቱን በተመለከተ በያሬዳዊ ጣዕመ ዜማ ‹‹ሃሌ ሉያ ተሣሃልከ እግዚኦ በእንተ ልደቱ ወጥምቀቱ ለክርስቶስ ማዕከለ ባሕር ገብአ ወወጽአ በሰላም›› በማለት ወርበዋል፡፡ መዘምራኑ እንደጨረሱ የእነሱን ፈለግ ተከትለው የወጡት የገዳሙ የሰንበት ት/ቤት ወጣቶችም ‹‹አጥመቆ ዮሐንስ ለኢየሱስ ወገሠሦ እንተ ኢትትገሠሥ ርእሶ›› የሚለውን ወረብ ካቀረቡ በኋላ የአጫብር ወረብ ቀርቧል።

ከዚህ በኋላ ለቃና ዘገሊላ ከሚመለሱት ሁለቱ የቅዱስ ሚካኤል ታቦታት በቀር ሌሎቹ ታቦታት መስቀል በያዙ ዲያቆናትና ጽንሐሕ በያዙ ካህናት ታጅበው በታላቅ ክብር በእልልታና በዝማሬ በተዘጋጀላቸው መድረክ ቆሙ፡፡ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ መልካም ፈቃድ ብፁዕ አቡነ ገሪማ የድሬዳዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና በጠቅላይ ቤተ ክህነት የውጭ ግንኙነት ኃላፊ በዓሉን በተመለከተ ሰፋ ያለ ትምህርትና መግለጫ ሰጥተዋል፡፡

kidstmaryamtimket12.jpg

በመጨረሻም ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ዕለቱን በተመለከተ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከምታከብራቸው ታላላቅ በዓላት ውስጥ አንዱ የሆነውን የጥምቀት በዓል ስታከብር በሚማርክና ለሌሎች አርአያ በሚሆን መልኩ እንደሆነና፥ ይህ መተሳሰብ፣ አርአያነትና ፍቅር ሌሎችን እየሳበ የበዓሉን አከባበር ሥርዓት ሊያዩና ሊካፈሉ ከአገር ውጭ የሚመጡት እንግዶቻችን ከዓመት ዓመት ቁጥራቸው እየጨመረ ነው። ለእንግዶችም ባስተላለፉት መልዕክት ወደዚህች አገር መጥተው ይህንን በዓል አብረው ማክበራቸው እድለኞች እንደሆኑና ሌሎችም ያላዩት እንዲያዩ እንዲያደርጉ አሳስበዋል፡፡ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ወጣቶችንም የአባቶቻቸውን ፈለግ ተከትለው የአባቶቻቸውን ሥርዓትና ሕግ ሳይለቁ የበለጠ እንዲሠሩ ሃይማኖታቸውን እንዲጠብቁ አሳስበዋል፡፡ ቃለ ቡራኬና ምዕዳን ከሰጡ በኋላ ታቦታተ ሕጉ በመጡበት አኳኋን ወደ መንበረ ክብራቸው በካህናት በሰንበት ት/ቤት ወጣቶችና በምዕመናን መዝሙር እየተዘመረ ተጉዘዋል፡፡

kidstmaryam.jpgበመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም የተገኙት የጠቅላይ ቤተ ክህነት ምክትል ሥራ አስኪያጅ ንቡረ እድ ኤልያስ አብርሃ በሰጡት ትምህርት «ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ማን አጠመቀው ብንባል ማን እንላለን? ዮሐንስ አጠመቀው እንበል? እኔ ግን ቅዱስ ዮሐንስ አምላክን በማጥመቁ የሰዎች ልጆች ሁላችን ነው ያጥመቅነው ብየ አምናለሁ። ኃይሌ ገ/ሥላሴ ሩጫ ቢያሸንፍ ኢትዮጵያ አሸነፈች እንደሚባለው፣ ሁሉም እንደሚደሰተው። «ተጠምቀ ሰማያዊ በእደ መሬታዊ» እንደተባለው ሰማያዊው አምላክ እግዚአብሔር ወልድ በመሬታዊው በዮሐንስ እጅ ተጠመቀ። ፈጣሪን የምናጠምቅ ሆነን አይደለም ምን ያህል እንደወደደን ያሳያል እንጂ። ብዙ ሰማያውያን ሠራዊት ነበሩ፣ በእነርሱ እጅ መጠመቅ ይችል ነበር፤ በባሕርይ አባቱ መጠመቅ ይችል ነበር፤ በባሕርይ ሕይወቱም መጠመቅ ይችል ነበር። ፈጣሪ አምላካችን በሰው እጅ ተጠመቀ እኮ? በእውነት ምን አይነት ፍቅር ነው? ምንስ አይነት መውደድ ነው? እኛም ፈጣሪ አምላክን ለማጥመቅ በቃን እኮ!» ብለዋል።

ታቦት እንተ ውስቴታ ኦሪት እንተ ውስቴታ….እልልልልልልልkidstmaryamtimket4.jpg

tmket.jpg

«እስመ ከመዝ ተድላ ለነ ወይደልወነ ከመ ንፈጽም ኲሎ ጽድቀ»

በተ/ሥላሴ ጸጋ ኪሮስ


tmket.jpgየጎንደር መንበረ መንግሥት መድኅኔዓለም ደብር አስተዳዳሪና የአራቱ ጉባኤያት /የብሉይ፣ የሐዲስ፣ የሊቃውንትና የመጻሕፍተ መነኮሳት/ የጉባኤ መምህር ከሆኑት ከሊቀ ሊቃውንት ዕዝራ ሐዲስ ጋር የጥምቀትን በዓል አስመልክተን በ09/05/03 ዓ.ም አጭር ቃለ ምልልስ በስልክ አድርገናል፡፡ ለሊቀ ሊቃውንት ዕዝራ ሐዲስ ከፍተኛ ምስጋናችንን እያቀረብን ለአንባቢዎቻችን የታላቁን ሊቅ ቃለ ምልልስ በማቅረብ እንኳን አደረሳችሁ እንላለን፡፡ መልካም ንባብ፡፡ 

አማርኛ መካነ ድር፡- ሊቀ ሊቃውንት እንኳን አደረስዎት?

ሊቀ ሊቃውንት ዕዝራ፡- እንኳን አብሮ አደረሰን።
 
አማርኛ መካነ ድር፡- ጤናዎት እንዴት ነው?

ሊቀ ሊቃውንት ዕዝራ፡- ደህና ነኝ እግዚአብሔር ይመስገን ደህና ነኝ።

timket3.jpgአማርኛ መካነ ድር፡- የጥምቀትን በዓል ለምን እናከብራለን? ለክርስቲያኖች ያለው ፋይዳ ምንድን ነው?

ሊቀ ሊቃውንት ዕዝራ፡- የጥምቀት በዓል መነሻው የጌታችን የመድኅኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ መጠመቅ ነው፡፡ ጌታችን ለምን ተጠመቀ ሲባል፣ መነሻው የአዳምና የሔዋን ድኅነት ነው፡፡ አዳምና ሔዋን ከአራቱ ባሕርያተ ሥጋና ከሦስቱ ባሕርያተ ነፍስ ተፈጥረው ከሥላሴ ልጅነትን ተቀብለው ዕፀ በለስን እንዳይበሉ ታዘው ለ7 ዓመታት ያህል የተሰጣቸውን አደራ ጠብቀው ከዕፀ በለስም ተቆጥበው ከቆዩ በኋላ በ7ኛው ዓመት ሰይጣን በእባብ አማካኝነት አትብሉ የተባሉትን ዕፀ በለስ በስሕተት እንዲበሉ አድርጎ፣ ዕፀ በለስን በመብላታቸው ምክንያት በሞተ ሥጋ ላይ ሞተ ነፍስ በርደተ መቃብር ላይ ርደተ ገሃነመ እሳት ተፈርዶባቸው 55ዐዐ ዘመን በመከራ መቆየታቸው ይታወቃል፡፡ ነገር ግን አዳምና ሔዋን ዕፀ በለሱን ከበሉ በኋላ እግዚአብሔር መሐሪ መሆኑን በመረዳት ንስሐ ገብተው ንስሐቸውን ሲጨርሱ እግዚአብሐር ተስፋ ሰጥቷቸዋል፤ ተስፋቸውም በሐሙስ ዕለት ወበመንፈቃ ለዕለት እትወለድ እም ወለተ ወለትከ፡፡ 55ዐዐ ዘመን ሲፈፀም ከልጅ ልጀህ ተወልጄ አድንሃለሁ ብሎ ተስፋ ስለሰጣቸው ይሄን ተስፋ ለመፈፀም መድኅኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሰማየ ሰማያት ወርዶ ከድንግል ማርያም በመጋቢት 29 ቀን ተጸንሶ ታኅሣሥ 29 ቀን ተወልዶ 3ዐ ዓመት ሲሞላው በ3ዐ ዓመቱ በዮርዳኖስ ተጠመቀ ለልደቱም ለጥምቀቱ ነቢያትን እያስነሳ ትንቢት አናግሯል፡፡ የተነገረው ትንቢትና የተቆጠረው ሱባኤ ሲፈፀም በዮርዳኖስ ወንዝ ተጠምቋል፡፡ ሲጠመቅም ለአዳምና ለሔዋን የተሰጠው ተስፋና ቃልኪዳን ተፈጽሟል፡፡

የአዳምና የሔዋን የእዳ ደብዳቤያቸው የኃጢአት ሰነዳቸው ተፍቋል፡፡ ስለዚህ የመድኀኔዓለም ክርስቶስ መጠመቅ ለዓለም በጠቅላላው ሕይወት መድኀኒት በመሆኑ የጥምቀት በዓል ከመጀመሪያው ጀመሮ እስከ አሁን ድረስ እየተከበረ ከዚህ ደርሷል፡፡ የጥምቀት በዮርደኖስ አዳም የዲያብሎስ የወንድ ተገዥ ሔዋን የዲያብሎስ የሴት አገልጋይ ብሎ ጽፎ በዮርዳኖስ ያስቀመጠውን የዕዳ ደብዳቤ ክርስቶስ ሲጠመቅ እንደ አምላክነቱ አቅልጦ እንደሰውነቱ ረግጦ አጥፍቶልናል፡፡ በሲኦል ያስቀመጠሙንም በአካለ ነፍስ ወደ ሲኦል ወርዶ አጥፍቶልናልና ጥምቀት ለክርስቲያኖች ያለው አስተዋጽኦና ፋይዳ ይሄን ይመስላል፡፡

አማርኛ መካነ ድር፡- የጥምቀት በዓል አከባበር እንዴት ተጀመረ? ጎንደር ላይ በልዩ ሁኔታ ይከበራል በዚህ መልክ መከበር የተጀመረውስ መቼ ነው?

ሊቀ ሊቃውንት ዕዝራ፡- የጥምቀት በዓል በኢትዮጵያ ሃይማኖታዊ ይዘቱና ክብሩ አንድ ነው፡፡ በመላው ኢትዮጵያ ሲጀመርም አንድ ላይ ነው የተጀመረው፡፡ ሃገራችን አንድ ጊዜ ነው ሃይማኖትን ጥምቀትን የተቀበለች፡፡ ስለዚህ አሁንም በገጠሩም በከተማም ታቦታቱ ወርደው በየወንዙ አጠገብ በድንኳን አድረው፣ የሚጸለየው ጸሎት፣ የሚቀደሰው ቅዳሴ የሚባረከው ባሕረ ጥምቀት ሁሉ አንድ ነው እና ጎንደርም ከኢትዮጵያ አንዷ ስለሆነች፣ የጥምቀቱን በዓል የጀመረችው በሰላማ ከሣቴ ብርሃን በመጀመሪያው ምእተ ዓመት ስለሆነ ከዚያ ጋር ልዩነት የለውም፡፡

እንግዲህ የጎንደር ጥምቀት ልዩነት አለው የሚባለውና በምን ጊዜ ተጀመረ ለሚለው ጥምቀተ ባሕሩ የጎንደር ከሌሎቹ ሁሉ ለየት ያለ ነው፡፡ ቦታው ማለት ነው። አፄ ፋሲለደስ ያሠሩት የጥምቀተ ባሕር መቅደስ አለ፡፡ ከቤተ መቅደሱ ግርጌ ደግሞ ባሕረ ጥምቀቱ አለ፡፡ ከአፄ ፋሲል ጀምሮ በዓሉ በዚያ ስለሚከበር ታቦታት እየወረዱ፥ ከቤተ መቅደሱ አድረው፥ እዚያው ተቀድሶ፥ ማኅሌቱም ተቁሞ ፤ ባሕሩም ደግሞ ሌሎቹ ሀገሮች ከሚጠቀሙበት ለየት ያለ ስፋትና ጥራት ያለው ሁልጊዜ እንደጸበል ከአንድ ቦታ ታቦታቱ ወርደው ማደራቸው በዓሉን በጎንደር ለየት ያደርገዋል፡፡

አማርኛ መካነ ድር፡-
በበዓሉ አከባበር የማኅሌትና የቅደሴ ሥርዓቱ አንዴት ነው? ከከተራ ጀምሮ?

ሊቀ ሊቃውንት ዕዝራ፡- ከእነ አፄ ፋሲል በፊት ቀሃ ኢየሱስ ቀዳሚ ደብር ነበር፡፡ የኢየሱስ ታቦት ፥ ቀሃ ወንዝ አለ ከዚያ ይወርዳል፡፡ ዛሬ የራሱ የኢየሱስ ታቦት ቤተመቅደስ ከተሠራበት ቦታ ድንኳን ተተክሎ ታቦቱ ከዚያ አድሮ ባሕረ ጥመቀቱ ቀሃ ወንዝ ነበር የሚባረከው፡፡ ኋላ ግን ከአፄ ፋሲለደስ ንግሥና በኋላ 44ቱ ታቦታት ከዚያ ይወርዳሉ፡፡
timket2.jpgድርቡሽ /Mahdists of sudan/ የጎንደርን አብያተ ክርስቲያናትን ካቃጠለ በኋላ ግን 8 ታቦታት ብቻ ይወርዳሉ፡፡ እነዚህም-
1.    መንበረ መንግሥት መድኀኔዓለም
2.    ደብረ ነገት አጣጣሚ ቅዱስ ሚካኤል
3.    ደብረ ጽባሕ እልፍኝ ጊዮርጊስ
4.    ደብረ ሰላም ፊት ሚካኤል
5.    ደብረ ብርሃን አባጃሌ ተክለ ሃይማኖት እነዚህ ከመሐል ከተማው ይወርዳሉ፡፡ ከታች ከባሕረ ጥምቀቱ አጠገብ ደግሞ
6.    የቀሃ ኢየሱስ
7.    የቅዱስ ፋሲለደስ
8.    የመጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ የላይኛዎቹን ጠብቀው አብረው ይገባሉ፡፡

ከዚያ በአንድ ላይ ማኅሌት ተቁሞ ያድራል፡፡ ማኅሌቱ ሲፈፀም የቅዳሴ ሥርዓት ይከናወናል፡፡ የባሕረ ጥምቀቱ የቡራኬ ሥርዓትም ይካሄዳል፡፡ ከዚያ ታቦታቱ ወጥተው ሃዲጎ ተስአ ወተስአተ ነገድ የሚለው ማኅሌታዊ ዝማሬ ተዘምሮ ሁለቱ የቅ/ ሚካኤል ታቦታት ከዚያው ይቆያሉ ሌሎቹ ግን በ7 ምዕራፍ ታቦታቱ እየቆሙ የማኅሌቱ ሥርዓት የዝማሬው ሥርዓት እየተካሄደ ወደየ መንበረ ክብራቸው ይመለሳሉ፡፡ በሁሉም የኢትዮጵያ ቤ/ክ አከባበር የማኅሌት ሥርዓቱ 7 ምዕራፍ አለው፡፡ ለእያንዳንዱ ምዕራፍም የተወሰነ ቀለም አለ፡፡

ጎንደርን ግን ለየት የሚያደርገው ማኅሌቱ የተደረሰው ጎንደር ላይ ነው ዛሬም ማስመስከሪያው ጎንደር በአታ ለማርያም ነው፡፡ የአቋቋሙ ምስክር መሆኑ የማኅሌቱ ምንጭ አጠቃላይ አቋቋሙ የተደረሰው እዚህ ስለሆነ ለየት ያደርገዋል፡፡ አንግዲህ የትርጓሜ መጻሕፍትና የአቋቋም ትምህርት መነሻው ጎንደር ስለሆነ ለየት ያደርገዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ በዕለቱ በሥርዓተ ቅደሴው ብዙ ምእመናን በቅዱስ ቁርባን ይሳተፋሉ፡፡

llEzraHaddis.jpg

አማርኛ መካነ ድር፡- የዘንድሮው የጥምቀት ክብረ በዓል ብዙ እንግዶች ይመጣሉ ተብሎ ይጠበቃል በሀገረ ስብከቱም ሆነ በእናንተ ጉባኤ ቤት ስብከተ ወንጌልን ለማስፋፋት አንዲሁም ቤተክርስቲያንን ለማስተዋወቅ ምን ያህል ዝግጅት ተደርጓል?

ሊቀ ሊቃውንት ዕዝራ፡-ይህ ነገር ቀደም ብሎ ታስቦበት ኮሚቴ ተዘጋጅቶ፤ ከሁለት ሳምንት ጀምሮ ለሕዝበ ክርስቲያኑ በዓሉ ሥርዓቱን ጠብቆ እንዲከበር በአለባበስም ሆነ አንግዳ በመቀበል ጥንታዊነታችን ኢትዮጵያዊነታችን ለማስመስከር ዝግጅት ተደርጓል፡፡ በስብከተ ወንጌልም ማንኛውም ሰው ወደ ንስሐ እንዲመለስ በመናፍቅነትም ወደ ሌላ ሃይማኖት የሄደ ካለ ቤተክርስቲያኑ ተመልሶ የቤተክርስቲያን ልጅ እንዲሆን ለሥጋ ወደሙ አንዲበቃ ቅስቀሳ ትምህርት ሲሰጥ ቆይቷል፡፡ አሁንም ምግባር ፣ ትሕትና፣ ፍቅር፣ እንግዳ መቀበል ብዙ ሰዎችን ያስተምራልና ለዚህ ሁሉ ሰባክያን ብቻ ሳይሆኑ ሕዝበ ክርስቲያኑ በእነዚህ ምግባራት ብዙ ሰዎችን እንዲስብ እየተደረገ ነው፡፡ ዛሬም በአጋጣሚ ክቡር ፕሬዜዳንት ግርማ ወ/ጊዮርጊስ ከሚኒስትሮች ጋር ገብተዋል ጥሩ አቀባበል ተደርጎላቸዋል፡፡

ጥምቀተ ባሕሩ ከሚከናወንበት ቦታ ላይ ሰባት ጎጆዎች ተዘጋጅተው የቤተክርስቲያናችን የአብነት ትምህርትን /ከፊደል ጀምሮ እስከ መጨረሻው ድረስ ያሉት የትምህርት ሥርዓቶች/ የሚያሳይ ኤግዚቢሽን ለክቡር ፕሬዚዳንቱና ለእንግዶች ገለጻ ተደርጓል፡፡ ይኽም ለሚቀጥሉት አምስት ቀናት ይቀጥላል፡፡

በማኅበረ ቅዱሳንም የተዘጋጀ ኤግዚቢሽን አለ፡፡ እርሱም በእንግዶች ተጎብኝቷል፡፡ የሀገራችን ገጽታ በዘመነ አበው፣ በዘመነ ኦሪት፣ እንዲሁም በዘመነ ወንጌል ከፋፍሎ የሚያሳይ ሲሆን ቤተክርስቲያኗ በሥነ ጽሑፍ፣ በመጻሕፍት፣በሥነ ጥበብ ያበረከተችውንም ሀብታት ይዳስሳል፡፡

በዘመነ ኦሪት መሥዋዕት የተሠዋባቸው ጥንታውያን ገዳማትና አድባራት በኤግዚቢሽን ቀርበው ገለጻ እየተደረገባቸው የሀገሪቱን ቀዳሚነትና ጥንታዊነት እያስተዋወቀም ይገኛል፡፡

 አማርኛ መካነ ድር፡- በመጨረሻም የሚያስተላልፉት መልእክት ካለ?

ሊቀ ሊቃውንት ዕዝራ፡- «እስመ ከመዝ ተድላ ለነ ወይደልወነ ከመ ንፈጽም ኲሎ ጽድቀ» ነው ያለ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፡፡ ከገሊላ መጥቶ ወደ ዮርዳኖስ በዮሐንስ እጅ ለመጠመቅ ሲቀርብ ዮሐንስ «ከሎ ወዐበዮ፤ አይሆንም እኔ ከአንተ እጠመቃለሁ እንጂ እኔ አንተን እንደምን አጠምቃለሁ፡፡» ሲለው ይህ ለእኔ እና ለአንተ ታላቅ ደስታችን ነው፡፡ የተነገረውን ትንቢትም ልንፈጽም ይገባናል፡፡  እኔ በአንተ እጅ ተጠምቄ ትሕትናዬ፤ አንተ እኔን አጥምቀህ ክብርህ ልዕልናህ ይገለጣል፤ ይህ ደስታችን ነው፡፡ ብሎ የአብ የመንፈስ ቅዱስን ከእርሱ ጋራ አንድ ባሕርይ አንድ ህልውና መሆናቸውን እንደገናም የእኛን ሥጋ በመዋሐዱ የእኛን ደስታ ለእርሱ የእርሱን ደስታ ለእኛ ሰጥቶ በማቴ.3.13 እንደተናገረው አሁንም ይህ የጥምቀት በዓላችን የእዳ ደብዳቤያችን የተፋቀበት፣ የተደመሰሰበት በዓል ስለሆነ በ40 ቀንና በ80 ቀን ተጠምቀው በክርስቶስ ክርስቲያን በወልድ ውሉድ የተባሉ ሁሉ የጥምቀት በዓልን ሲያከብሩ የራሳቸው ነጻነት ልጅነት የተመሠረተበት መሆኑን በመረዳት በደስታና በፍቅር ማክበር ይገባል፡፡

ይህ በዓል የነጻነት በዓል፣ የኃጢአት የቁራኝነት የፍዳ ደብዳቤ የጠፋበት ስለሆነ፣ ዛሬም ማንኛውም ሰው ከኃጢአት ወደ ጽድቅ ተመልሶ ከፍዳ መርገም ወደ በረከት ተመልሶ ለሥጋው ለደሙ በቅቶ ፈጣሪው ጋር ተገናኝቶ፣ በዓሉን ካከበረ በዚህ ዓለም ያከበረውን በዓል ኋላም በመንግሥተ ሰማያት ከመላእክት ጋር ለማክበር ዕድሉ ስለተሰጠው ሰው ሁሉ በዚህ በዓል ሊጠቀምበት ይገባል፡፡

እንግዲህ ለመላው ሕዝበ ክርስቲያን በውጭም በሀገር ውስጥም ለሚኖሩ ሁሉ የጥምቀት በዓል የሰላም የበረከት የፍቅር በዓል እንዲሆንልን እንኳን በሰላም አደረሳችሁ አደረሰን፡፡ የሰላም ባለቤት ኢየሱስ ክርስቶስ በመካከላችን ተገኝቶ በዓሉን በሰላም አስጀምሮ በሰላም እንዲያስፈጽመን ዛሬ በዚህ ዓመት በዓሉን ለማክበር የፈቀደልን ከርሞ በሰላም ደርሰን በዓሉን ለማክበር እንዲያበቃን የታመሙትን እንዲፈውስልን፣ የወጡትን በሰላም እንዲመልስልን ሀገራችንን በምሕረቱ፣ በይቅርታው እንዲጎበኝልን ዓለምን በጠቅላላው በዓይነ ምሕረቱ ተመልክቶ ለዓለም ምሕረቱን እንዲልክልን የአምላካችን ፈቃዱ ይሁንልን፡፡

አማርኛ መካነ ድር፡- እግዚአብሔር ይስጥልን በዕድሜ በጸጋ ይጠብቅልን፡፡

ሊቀ ሊቃውንት ዕዝራ፡– አሜን፡፡
 
ወስብሐት ለእግዚአብሔር