የምእመናን መሰባሰብ፤ የቅዳሴ ቀዳሚ ምስጢር

ታኅሣሥ 13/2004 ዓ.ም

በዲ/ን በረከት አዝመራው

ቅዳሴ የአንዲቷ ሰማያዊት ቤተ ክርስቲያን እውነተኛ ገጽ እንደሆነ ሁሉ የምእመናን መሰባሰብ ደግሞ የቅዳሴ የመጀመሪያ መሠረት ነው፡፡ kidaseበመሰባሰብ የፈጸመው የቅዳሴ ሥርዓታችን አስቀድሞም በቅዱሳን መላእክት ዓለም የነበረና በምድር ባለች መቅደሱም በምእመናን መሰባሰብ የሚፈጸም ነው፡፡ “እኔ በመካከላቸው እሆናለሁ” ብሎ ደስ የሚያሰኝ ዘላለማዊ ቃል ኪዳን የገባልን ጌታችን፣ “ሁለት ወይም ሦስት በስሜ በሚሰበሰቡበት” በማለት መሰባሰባችን ጸጋና ረድኤቱን እንድናገኝ ምክንያት መሆኑን ነግሮናል /ማቴ.18፥20/ በዚህ ርዕስም የጌታን ቃል በታላቅ ትጋት በፈጸመች ሰማያዊ ሥርዓቷን ከቅዱሳን መላእክት ዓለም ያገኘች፣ የምስጋና ሥርዓቷም በትውፊት ደርሶ ለቤተ ክርስቲየን መሠረት በሆነው በጠንታዊት /በሐዋርያት ዘመን/ ቤተ ክርስቲያን ለምእመናን መሰባሰብ ይሰጥ የነበረውን ትኩረትና ምስጢራዊ እይታ እንመለከታለን፡፡

 

የምእመናን መሰባሰብ በቅዳሴ ጥንታዊ ትውፊት

ተሰባስቦ እግዚአብሔርን ማመስገን መሥዋዕትን ማቅረብ አስቀድሞ በብሉይ ኪዳንም በምሳለ የቆየ ቢሆንም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሐዋርያት ጋር በቤተ አልዓዛር የአይሁድን ፋሲካ ሲያከብር የአማናዊው ቅዳሴ መሠረት ተጣለ /ሉቃ.22፥7/፡፡ የቤተ እስራኤል ጉባኤ መሠረት ይሆኑ ዘንድ ዐሠራ ሁለቱን የያዕቆብ ልጆች የመረጠ እግዚአብሔር እስራኤል ዘነፍስ የተባሉ የምእመናን ጉባኤ የሆነች የቤተ ክርስቲያን መሠረቶች የሆኑ ሐዋርያትን ሰብስቦ በመንግሥተ ሰማያት ማዕድ ላይ አስቀመጣቸው /ሉቃ.22፥29-30/፡፡ በዚህም በሐዋርያት በኩል የቤተ ክርስቲያን አንድነት መመሠረቱን እንመለከታለን፡፡ በመንፈስ ቅዱስ መምጣት /ጸጋውን ረድኤቱን በመቀበል/ የጌታን ምስጢር ሁሉ የተረዱት ሐዋርያት አባቶቻችንም የቅዳሴን ምስጢር ምእመናንን ሰብስበው በአንድነት የሚፈጽሙ ሆነዋል /የሐዋ.20፥2/፡፡
ይህ ሥርዓት በሐዋርያዊት ቤተ ክርስቲያን በእርግጥም የጸና ሆኗል፡፡ “ለእናንተ ደግሞ አሳልፌ የሰጠሁትን እኔ ከጌታ ተቀብያለሁና” የሚለው ሐዋርያው ቅዱስ ጳዉሎስ “በመጀመሪያ ወደ ማኅበር ስትሰበሰቡ…” በማለት በእርሱ ዘመን የምእመናን መሰብሰብ ለዐበይት ሃይማኖታዊ ሥርዓቶች ቅድመ ሁኔታ እንደነበረ ይናገራል /1ቆሮ.11-18/፡፡ “ለእናንተ ደግሞ አሳልፌ የሰጠሁትን እኔ ከጌታ ተቀብያለሁና” በማለቱም ይህ በሥርዓተ ቅዳሴ በቤተ ክርስቲያን የመሰባሰብ ምስጢር ከዚያ በኋላ ሥርዓቱን ጠብቆ በትውፊት የሚተላለፍ ሆኗል፡፡
የሐዋርያት ተከታዮች የሆኑ አበውም ይህን የሐዋርያት ትውፊት ተቀብለው በቀጥታ ለትውለድ አስተላልፈዋል፡፡ ይህንንም “ትምህርታችን ከቅዳሴ ጋር የተስማማ ቅዳሴያችንም ትምህርታችንን የሚያጸና ነው” ብለው አጽንተውታል፡፡ /St. Iranaeus, Against Heresies 4:18-5/ /ማቴ.18፥ 20/፡፡

በዚህ ዘመን ምእመናን ሁሉ በቅዳሴ ተገኝተው ሁሉም ሥጋወደሙ ተቀብለው ይሔዱ ነበር፡፡ የታመመ እንኳ ቢኖር ሔደው ያቀብሉት ነበር፡፡ ያለሕማምና ከባድ ችግር ቅዳሴ የቀረ ሰው ራሱን አውግዞ ከቤተ ክርስቲያን እንደለየ ይቆጠር ነበር /fr.Alexander Schmemann, Eucharist, pp.24/፡፡

ሥርዓተ ቅዳሴ የሁሉም ምስጢራተ ቤተ ክርስቲያን ሕንፃም ይህን ለማስፈጸም አመቺ ተደርጐ ይሠራ ነበር፡፡ ይህ ጥንታዊ የሕንፃ ቤተ ክርስትያን አሠራር ትውፊት አሁንም በቤተ ክርስቲያናችን በግልጽ ያለ ነው፡፡ ቅዳሴ ወንዶች፤ ሴቶች፣ ሕፃናት ሁሉ ሊሳተፉት የሚገባ ምስጢር ባይሆን በቤተ ክርስቲያን ካህናት፣ ወንዶች፣ ሴቶች የሚቆሙበት ቦታ ለይቶ ማዘጋጀት ለምን ያስፈልግ ነበር? ይህ የሆነው ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ፣ የክርስቶስ አካል የሆነች የምእመናን አንድነት ማሳያ ስለሆነ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን የክርስቶስ አካል ናት ስንል ሁሉንም ምእመናን አቅፋ የያዘች መሆኗን እንደሚገልጽ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን የዚህ መገለጫ ከሆነ ሁሉን ሊይዝ ይገባዋልና፡፡

በቅዳሴ ጊዜ ስላለው የምእመናን ኅብረት /ስብስብ/ የጥንታዊት ቤተ ክርስቲያን እይታ ከዚህም የመጠቀ ነበር፡፡ በጥንታዊት ቤተ ክርስቲያን የምእመናን ስብስብ ምድራውያንን ብቻ ሳይሆን ሰማያውያንንም ያጠቃለለ እንደሆነ ይታመን እንደነበር በምርምር በተገኙ ጥንታውያን ሥዕሎች ይታያል፡፡ በልባዊ እምነታቸው በጥልቀት ያለውን የእነርሱን እና የሰማያውያንን ኅብረት በሥዕል ያሳዩ ነበር፡፡ አንድ የነገረ ቤተ ክርስቲያን ሊቅ ይህን ሲገልጹ “በብዙ ጥንታውያን አብያተ ክርስቲያናት ሥዕላቱ ከማኅበረ ቤተ ክርስቲያን ጋር የሚሳተፉ፣ የዚህን ምስጢር ትርጉም የሚናገሩ፣ ዘላለማዊ እንቅስቃሴውንና መስመሩን የሚያሟሉ እንደሆነ እንረዳለን” ይላሉ /Alexander schememann. The Euchrist pp.21/
ይህ ሥርዓት አሁንም በቤተ ክርስቲያናችን ይታያል፤ ይጠበቃልም፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን ጥንታዊ ትውፊት መሠረትም ቅዱሳት ሥዕላት ቅድስትና መቅደሱን በሚለየው ግድግዳ ላይ ይሣላሉ፡፡

ከዚህም በተጨማሪ ሌላ ምስክር አለን፡፡ ሥርዓተ ቅዳሴአችን ይዘቱና አፈጻጸሙ እንደሚያመለክተን እያንዳንዱ የካህን ጸሎት እየንዳንዱ የዲያቆን ትእዛዝ በምእመናን መልስ /አሜን/ ይጸናል፤ ይፈጸማል፡፡ በመጽሐፈ ቅዳሴ የምናነበው “ይበል ካህን፣ ይበል ሕዝብ…” የሚሉት ትእዛዛትም ለዚህ ምስክር ናቸው፡፡ በዚህም ሥርዓተ ቅዳሴ የካህናት ብቻ ሳይሆን የምእመናንና የካህናት የአንድነት ምስጢር መሆኑን እንረደለን፡፡

ይህንን የአንድነት ምስጢር ለማጽናት በፍትሐ ነገሥቱ ስለቅዳሴ በተነገረበት ክፍል “ምእመናን ሳይሰበሰቡ ቅዳሴ የሚጀምር አይኑር” የሚለው መልእክት እዚህ ላይ ልብ ይሏል፡፡

በዘመናችን የሚታየው የቅዳሴን ለካህናትና ለተወሰኑ ሰዎች መተው፣ ለቤተ ክርስቲያን ሥርዓትና የሕይወት ልምድ እንግዳ የሆነ ስርዋጽ ነው፡፡ አንዳንዶች ሥርዓተ ቅዳሴ በዋነኝነት የካህናት ሥራ እንደሆነ እና እነርሱ ግን ቢኖሩም እንኳን አዳማጭ፣ አዳማቂ እንደሆኑ ያምናሉ፡፡ ይህ አስተሳሰብ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ከውስጧ ከሚሰሟት ሕመሞች አንዱ ነው፡፡ አንዳንዴ ለሚታየው በሥርዓተ ቅዳሴ በንቃት አለመከታተል፣ ከዚህም የተነሣ የመንፈሳዊ ሕይወት መድከም፣ አንዱ ምክንያት መሆኑን መረዳት ይገባል፡፡

የመሰባሰባችን ምስጢር

የምእመናን አንድነት፣ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የክርስቶስ አካል ናት፡፡ እያንዳንዱ ምእመን ደግሞ የክርስቶስ ብልት ነው /1ቆሮ.12፥27/፡፡ እንግዲህ በምእመናን መሰባሰብ፣ ከምድራዊ አስተዳደራዊ ተቋም በተለየ የላቀች ቅድስት የሆነች የክርስቶስ አካል፣ የቤተ ክርስቲያን የአንድነቷ የቅድስናዋ ታላቅ መዓርግ /ፍጻሜ/ ይሆናል፡፡

“የቤተ ክርስቲያን ፍፁምነት” ማለትም ቅድስት የሆነች የቤተ ክርስቲያን በሰማያዊ ገጽታዋ መገለጥ ማለት ነው፡፡ የምእመናን ስብሰብ እንደማንኛውም ምድራዊ ስብስብ የሺህዎች “ድምር” ማለት ሳይሆን የክርስቶስ ሰማያዊ አካል /በስሙ በማመን ብልቶቹ የሆኑ ምእመናን ኅብረት/ መገለጥ ነውና፡፡

ብዙ የቤተ ክርስቲያንን ጥንታዊ ትውፊቶች የማይቀበሉ አዳዲስ የሥነ መለኮት አስተምህሮዎች ብቅ ብቅ ባሉበት በዘመናችን ይህን ጠንቅቀን ማወቅ ይገባናል፡፡ እነዚህ ምድራውያን አስተምህሮዎች ለአምልኮ ሥርዓት ግድ የሌላቸው፣ ቢኖራቸው እንኳ አንዱን የቅዳሴ ክፍል ከሌላው የሚያበላልጡ፣ አንዱን በጣም አስፈላጊ አንዱን ደግሞ ብዙም የማያስፈልግ አያደረጉ መመደብ የሚቀናቸው ናቸው፡፡ ስለቅዳሴ ብንጠይቃቸው ሕብስቱና ወይኑ የሚለወጥበትን ጊዜ አጉልተው ሌላውን አሳንሰው የሚናገሩ ናቸው፡፡ ሕብስቱና ወይኑ የመለወጡን ነገርም ቢሆን በኦርቶደክሳዊና ሰማያዊ መንገድ ሳይሆን በሳይንሳዊና ምድራዊ መንገድ ለማረጋገጥና ለመተንተን የሚፈልጉ ናቸው፡፡ እነዚህ አስተምህሮዎች በቅዱሳት መጻሕፍት ተቀባይነት የሌላቸው ናቸው፡፡

ይህን ሰማያዊ ምስጢር የምታውቅ ጥንታዊት ቤተ ክርስቲያን የአንድ ምእመን ከቅዳሴ መቅረት በጣም ያስጨንቃት ነበር፡�The Eucharist, pp21/

የቤተ ክርስቲያን ቅድስና ይህ ነው፤ የክርስቶስ አካል መሆኗ፡፡ እያንዳንዳችን ምንም ያህል ኀጢአተኞች ልንሆን እንችላለን፤ ነንም፡፡ የምእመናን አንድነት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ግነ ንጽሕት ቅድስት ናት፡፡ ይህም ከእኛ የመጣ ቅድስና ሳይሆን አካሉ በሆነች በቤተ ክርስቲየን “ራሷ” ሆኖ በመካከላችን ካለው ክርስቶስ የተገኘ ነው፡፡ ከኀጢአት የማንጠራ /የማንርቅ/ ጎስቋሎች ብንሆንም በመሰባሰባችን “የምትመሠረት” ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ግን በእውነት ንጽሕት ናት፤ የሕመሟ መድኀኒት፣ የቅድስናዋ ምንጭ በመካከሏ ነውና፡፡ በምእመናን መሰባሰብ “የተገነባች” ቤተ ክርስቲያን “ቅዱስ ሕዝብ፣ የንጉሥ ካህናት፣ የተመረጠ ዘር….” መባል ይገባታል፤ የመረጣት ከኀጢአት ባርነት አውጥቶ ያከበራት የቅድስናዋ አክሊል በመካለሏ ነውና /1ጴጥ.2፥9/፡፡ ለዚህ ነው በሐዋርያት ዘመን የነበሩ ምእመናን “ቅዱሳን” ይባሉ የነበሩት፤ በመሰባሰብ ይኖሩ ነበረና /ፊልሞ.1፥7/፡፡

ይህ መሰባሰብ የቅድስና መዓዛ ነው፡፡ ይህ ሰማያዊ ደስታ ነበረ መራራውን መከራ በደስታ እንዲቀበሉት ያስቻላቸው፡፡ ይህ የቅድስና ጉባኤ የቤተ ክርስቲያን ሰማያዊ ደስታ ነበር፡፡ በአስቸጋሪው ዓለም ክርስትናን በቆራጥነት እንዲሰብኩ ያስቻላቸው ታላቅ አንድነት ከዚህ የመነጨው ፍቅረ ቢጽና ፍቅረ እግዚአብሔር ነው፡፡ “ፍፃሜ ማኅበርሃ ለቤተ ክርስቲያን፣ የቤተ ክርስቲያን የማኅበሯ ፍጻሜ” ይህ ነውና፡፡

የምእመናን መሰባሰብ የክርስቶስን አካል እንደሚገልጥ፣ ቅዳሴውን የሚመራው ካህን ራስ የተባለ የክርስቶስን ክህነት ይገልጣል፡፡ /ኤፌ.5፥23፣1ቆሮ.11፥3/ በጸጋ በተሰጠው ሥልጣነ ክህነት ውስጥ ሆኖ /እያገለገለ// የክርስቶስን የባህርይ /ዘላለማዊ/ ክህነት ይመሰክራል፡፡ ካህኑ የሚለብሰው የክህነት ልብስ፣ ክርስቶስ በውስጧ ያደረው የቤተ ክርስቲያን መገለጫ ነው፡፡ ለዚህ ነው በቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ምእመናን ሳይሰበሰቡ ልብሰ ተክህኖ መልበስ የተከለከለው፡፡ /መጽሐፈ ቅዳሴ/ በካህኑ ራስ ላይ ያለው አክሊል እንደ መልከ ጸዴቅ ሥርዓት ያለውን ዘለዓለማዊውን የክርስቶስ ክህነት ይመሰክራል፡፡ /ዕብ.7፥20-22፣ መዝ.109፥4፣ ዕብ.7፥1/ እንግዲህ የጌታችን ዘለዓለማዊ ክህነት በዘለዓለማዊና ሰማያዊ መቅደሱ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን /በምእመናን መካከል/ በዚህ መልኩ ይገለጣል፤ ቅዱስ ጳዉሎስ “እርሱ ግን የማይለወጥ ክህነት አለው” እንዳለ /ዕብ.7፥25/፡፡ ስለዚህ መሰባሰባችን ክርስቶስን በመካከላችን አድርገን ነው፡፡ ስለዚህ በቅዳሴ መሰባሰባችን በመካከላችን ካለው ከመድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተነሣ በእውነት ታላቅ ነው፡፡

በመጨረሻ፣ እግዚአብሔር በማያሳየው ምድር በደስታ ይኖር ዘንድ አብርሃም ወገኖቹንና የአባቱን ቤት እንዲተው ከታዘዘ ወደ እግዚአብሔር መገለጫ፣ ወደ ጽዮን ተራራ ስንወጣ፤ የበኩራትን ማኅበር ልንመሠርት ስንሰባሰብ እንዴት ዓለማዊ ጣጣችንን አንተው? እስራኤል በሲና ተራራ በሚያስፈራ ሁኔታ የተገለጠውን እግዚአብሔርን ለመስማት ሦስት ቀን ከተዘጋጁ፤ ልብሳቸውን ካጠቡ፤ በሚያስደንቅ የመሥዋዕትነት ፍቅሩ ስለኛ የተሰቀለውን አምላካችንን ለማየት ብቻ ሳይሆን ለመብላት ለመጠጣት ስንሰባሰብ ምን ያህል መዘጋጀት፣ ልብሳችን ብቻ ሳይሆን ሥጋውንና ደሙን ሰውነታችንን ምን ያህል በንስሐ ማጠብ ይገባን ይሆን? /ዘፍ.12፥1፣ ዕብ.12፥22-24፣ ዘፀ.19፥14-15/ ሕፃኑ ሳሙኤል በቤተ መቅደስ ለሚጠራው ቃል በንቃት መልስ ከሰጠ፤ በእውነተኛ ቤተ መቅደሱ የተሰበሰብን እኛ በቅዳሴ ሰዓት በልዩ ልዩ መንገድ ለሚሰማው የእግዚአብሔር ድምፅ ምን ያህል በትጋትና በንቃት መልስ መስጠት ይኖርብን ይሆን? /1ኛ. ሰሙ.3፥1-14/ በእውነት እግዚአብሔር ከዚህ ሰማያዊ ጉባኤ አይለየን፡፡ ዛሬም ዘወትርም ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

ምንጭ፡- ሐመር 17ኛ ዓመት ቁጥር 6 ኅዳር/ታኅሣሥ 2002

 

ልዩ ዐውደ ጥናት

Gedamat Awude Tinat04

ለአንተ እንዲደረግልህ የምትፈልገውን ለሌላውም አድርግ

ሰዎች በኑሮአቸው ሁልጊዜ እንዲፈጽሟቸው በቅዱስ መፅሐፍ ከተቀመጡ መንፈሳዊ ተግባራት ውስጥ፡

  • የተራበን ማብላት፣
  • የተጠማን ማጠጠት፣
  • የታረዘን ማልበስ
  • በአጠቃላይ ለሰዎች ሁሉ በጎ ነገርን ማድረግ ናቸው፡፡

ይህን የተቀደሰ ነባር መንፈሳዊ ተግባር አጠናክሮ ለመቀጠል እና የተቸገሩ ወገኖቻችን ለመርዳት፣ “ለአንተ እንዲደረግልህ የምትፈልገውን ለሌላውም አድርግ” በሚል ርእስ በችግር ላይ ያሉ ወገኖቻችን ማኅበራዊ ህይወት ለመደገፍ እና ራሳቸውን ችለው ህይወታቸውን መምራት እንዲችሉ ለማድረግ የሚያስችል ሲፖዚየም ተዘጋጅቷል፡፡
በሲንፖዚየሙ ላይ

  • በማኅበራዊ ዘርፍ ከፍተኛ አገልግሎት ከሚሰጡ ተቋማት ተሞክሮ ይቀርባል፡፡
  • በሁለት ልብሶች መርሐ ግብር ድጋፍ የተደረገላቸው አካላትን አስመልክቶ በፊልም የተደገፈ መረጃ ይቀርባል፡፡
  • በማኅበራዊ ዘርፍ ጥናትና ምርምር ያደረጉ ሊቃውንት ልምዳቸውን ያካፍላሉ፡፡

አዘጋጅ፡-በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ሰ/ት/ቤቶች ማ/መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን
ቦታ፡- በጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ
ቀን፡- ታህሣሥ 22 ቀን 2004 ዓ.ም
ስዓት፡-7፡30-11፡00
ስልክ 011 1 55 36 25

ለደቡብ ትግራይ ማይጨው እና ደቡብ ምሥራቅ ትግራይ አህጉረ ስብከት ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና ካህናት ሥልጠና በመሰጠት ላይ ነው፡፡

ታኅሣሥ 5/2004 ዓ.ም

በዲ/ን ኅሩይ ባየ

ሥልጠናው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በደቡብ ትግራይ ማይጨውና ደቡብ ምሥራቅ ትግራይ አህጉረ ስብከት እንዲሁም በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን በዋናው ማእከል ምክክር የተዘጋጀው ነው፡፡

ከታኅሣሥ 2 ቀን 2004 ዓ.ም ጀምሮ በደቡብ ትግራይ ሀገረ ስብከት መንበረ ጵጵስና አዳራሽ በማይጨው ከተማ ከ 11 ወረዳዎች ለተወጣጡ 150 ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና ካህናት ሥልጠና እየተሰጠ መሆኑን የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ አስታወቁ፡፡ ከታኅሣሥ 2 እስከ 6 ቀን 2004 ዓ.ም በሚቆየው በዚህ ሥልጠና የተገኙት የወረዳ ቤተ ክህነት ሊቃነ ካህናት፣ የአብነት መምህራን፣ የገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎች መሆናቸውን ብፁዕነታቸው ገልጠዋል፡፡

ሥልጠናው በተሳካ መልኩ እንዲከናወን ሀገረ ስብከቱ የቅድሚያ ዝግጅት ማድረጉን ያስታወቁት ብፁዕነታቸው “ከአዲስ አበባ ተነሥታችሁ በማታውቁት መንገድ አስፋልቱን መሪ አድርጋችሁ ወደ ማይጨው ሀገረ ስብከት የመጣችሁ ልጆቻችን እንኳን ደኅና መጣችሁ፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን የቤተ ክርስቲያን አባልና አካል የሆነ ማኅበር ነው፤ ስለ ማኅበረ ቅዱሳን በቂ ግንዛቤ የሌላቸው ወገኖቻችን የተለያየ አሉባልታ ሊያስወሩ ይችላሉ፣ እናንተ ግን በቤተ ክርስቲያን ላይ እየተከናወነ ያለውን ሤራ ለማስቆም እንደምትሮጡ ምስክሮቹ እኛ ነን፡፡ ቅን አገልግሎታችሁን ስለተገነዘብን ሓላፊነቱን ወስደን ይህን ሥልጠና በጋራ አዘጋጅተናል፡፡ የጤፍ ዘር ለመልቀም አልመቸው ያለ ዝንጀሮ ከዳር ላይ ቆሞ ‘ጤፍን የዘራ ገበሬ ገበሬ አይባልም’ አለ እንደሚባለው ማኅበረ ቅዱሳንም ሤራችንን ያውቅብናል ብለው የሚሠጉና የሚፈሩ ተሐድሶ መናፍቃን በኑፋቄ ትምህርታቸው ብዙዎችን ለማሰናከል የሚያደርጉትን የጥፋት ሥምሪት ከነላኪዎቻቸው ስለምታውቁባቸው ላትስማሟቸው ትችላላችሁ፡፡ እውነተኛ ዓላማ ያላቸው የቤተ ክርስቲያን አባቶች በጸሎት፣ በሃሳብና በቅን ምክራቸው እንደማይለዩዋችሁ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን ጉባኤያችንን ይባርክልን” ሲሉ አባታዊ ቃለ ምዕዳናቸውን አስተላልፈዋል፡፡

በተጨማሪም የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ መልአከ ምሕረት አባ ዘካርያስ ሕሉፍ ባስተላለፉት መልእክት «ካህናት የተሰጣችሁን አደራ በትክክል እንድትወጡና ዘመኑን በመዋጀት እንድታስተምሩ አሳስባለሁ፡፡ ይህ ሥልጠና የመመካከሪያ መርሐ ግብር በመሆኑ በንቃትና በትጋት ሥልጠናውን እንድትከታተሉ አደራዬ ጥብቅ ነው፡፡ መርሐ ግብሩን አመቻችቶ መምህራንን ከአዲስ አበባ በመላክ፣ መጻሕፍት፣ ደብተር፣ እስክሪቢቶ፣ የሠልጣኞችን የምሳ ወጪ እና የውሎ አበል በመሸፈን ማኅበረ ቅዱሳን ስላበረከተው መንፈሳዊ ድጋፍ ምስጋናዬን አቀርባለሁ» ብለዋል፡፡

ታኅሣሥ 2 ቀን የተጀመረው ሥልጠና በተያዘለት መርሐ ግብር መሠረት የተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴ፣ የነገረ ሃይማኖት መግቢያ፣ አእማደ ምሥጢራት፣ ነገረ ድኅነት፣ ነገረ ቅዱሳን እና የቤተ ክርስቲያን ታሪክ እንደሰጡ ተገልጧል፡፡

ሥልጠናው በተጀመረበት ዕለት ስለ ተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴ በስፋትና በጥልቀት ተዳስሷል፡፡ መናፍቃን በቤተ ክርስቲያን ላይ ያከናወኑት ሴራ ምን ያህል ከባድና አሳዛኝ እንደ ሆነ የተደረሰበት የጽሑፍ፣ የምስልና የድምጽ መረጃ ለካህናቱ ቀርቧል፡፡ ሠልጣኝ ካህናቱም መናፍቃን መልካቸውን እየቀያየሩ ሃይማኖታችንን ለማስነቀፍ የእኛን ቀሚስ ለብሰው፣ አስኬማችንን ደፍተው፣ መነኮሳትና ባሕታውያን እንዲሁም አጥማቂዎች መስለው በወርሐ ጾም በየሥጋ ቤቱ እየገቡ ሆን ብለው ሥጋ እየበሉ በአከባቢያችን የታዩ ተሐድሶ መናፍቃን ነበሩ ሲሉ ካህናቱ በዓይናቸው ያዩዋቸውንና በተግባር የገጠሟቸውን የተለያዩ ክሥተቶች በተጨባጭ መረጃ በቁጭት ተናግረዋል፡፡

በተሰጠው መረጃ የመናፍቃኑ ተልእኮ ለቤተ ክርስቲያን ፈተና መሆኑን በጥልቀት እንደ ተገነዘቡ የገለጡት ካህናቱ ክህነታዊ ሓላፊነታቸውን በአግባቡ በመወጣት ሕዝበ ክርስቲያኑን በማስተማር አደራቸውን እንደሚወጡ አስታውቀዋል፡፡

ሦስተኛ ቀኑን ያስቆጠረው ሥልጠና የፊታችን ዓርብ እንደሚጠናቀቅ ይጠበቃል፡፡

“የእግዚአብሔር ቤት” በሚል ርእስ የተሠራው የኢየሱስ ክርስቶስ የስቅለት ፊልም ከቀኖና ቤተ ክርስቲያን ውጭ እንደሆነ ተገለጠ፡፡

ኅዳር 28/2004 ዓ.ም.
በዲ/ን ኅሩይ ባየ

የእግዚአብሔር ቤት /The abode of God/ በሚል ርእስ በጀርመናዊቷ ሚስስ ብሪጅት ማሪያ ማየር ተዘጋጅቶ በተወሰኑ ኢትዮጵያዉያን አርቲስቶች የተሠራው የኢየሱስ ክርስስቶስ የስቅለት ፊልም ከቤተ ክርስቲያን ቀኖና እና ትውፊት ውጭ እንደሆነ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሊቃውንት ጉባኤ ኅዳር 28 ቀን 2004 ዓ.ም የሰጠው መግለጫ ያስረዳል፡፡

 

ሚስስ ብሪጅት ማሪያ ማቶር የተባለችው ጀርመናዊት በኢትዮጵያውያን የኪነ ጥበብ ሰዎች እንዲሠራ ያዘጋጀችው ፊልም በይምርሐነ ክርስቶስ፣ አሸተን ማርያምና በጉንዳጉንዶ ገነተ ማርያም አብያተ ክርስቲያናት ተቀርጾ ለዕይታ እንዲቀርብ የመንግሥት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤት ያቀረቡት ጥያቄ ጉዳዩ ሃይማኖታዊ ስለሆነና ቀረጻው የሚካሔድበት ቦታ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲየን አብያተ ክርስቲያናት ስለሆነ ጉዳዩ በቤተ ክርስቲያኗ እንዲታይና እንዲፈቀድ ማሳሰቢያ ሰጥቷል፡፡

ከመንግስት ኮሚዮኒኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤት በተሰጠው አስተያየት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽሕፈት ቤት በቁጥር ል/ጽ/565/279/03 በቀን 8/11/2003 ዓ.ም በሊቃውንት ጉባኤ እንዲታይ የፊልሙ ጽሑፍ ቀርቧል፡፡ የሊቃውንት ጉባኤውም በተሰጠው መመሪያ መሠረት ከ11/11/2003 እስከ 15/11/2003 ዓ.ም ለአምስት ተከታታይ ቀናት ባደረገው ጉባኤ 80 ገጾች ያሉትን የፊልም ጽሑፍ መርምሮ የውሳኔ ሐሳቡን ለቋሚ ሲኖዶስ አቅርቧል፡፡

ቋሚ ሲኖዶስም ጳጉሜን 1 ቀን 2003 ዓ.ም ባደረገው ጉባኤ በሊቃውንት ጉባኤ የቀረበውን የውሳኔ ሐሳብ መርምሮ የተዘጋጀው የፊልም ጽሑፍ፡-

• የክርስቶስን ቅዱስ ወንጌል በአግባቡ የማይገልጽ በመሆኑ፣ የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት፣ ትውፊትና ታሪክ ባለመጠበቁ፣ የኢየሱስ ክርስቶስን አምላክነት መከራ መስቀሉን፣ ሕማሙን፣ ሞቱንና ትንሣኤውን ዝቅ አድርጎ በማቅረቡና ባጠቃላይ ከቤተ ክርስቲያናችን ትምህርተ ሃይማኖት፣ ቀኖና ትውፊት ውጭ ስለሆነ የፊልሙ ጽሑፍ ውድቅ ሆኗል ሲል ውሳኔ አስተላልፏል፡፡

 

በቋሚ ሲኖዶስ በተሰጠው ውሳኔ መነሻነት የመንበረ ፖትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት በቁጥር 7403/2789/2003 በቀን 18/11/2003 ዓ.ም ቀረጻው ሊካሔድበት ለታሰቡት አህጉረ ስብከቶች ማለትም ለትግራይ ምሥራቃዊ ዞን ሀገረ ስብከትና ለሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት ጽ/ቤት ፊልሙ እንዳይሠራና ቀረጻው ተጀምሮ ከሆነም ቀረጻው እንዲቆም በደብዳቤ አስታውቋል፡፡

 

የመንበረ ፖትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት የፊልሙን ኢ-ሥርዐታዊነት ገልጦ መስከረም 4 ቀን 2004 ዓ.ም ለጀርመን ኢምባሲ፤ መስከረም 11 ቀን 2004 ዓ.ም ደግሞ በኢትዮጵያ ውስጥ ላሉ አህጉረ ስብከቶች በደብዳቤ መግለጡን የሊቃውንት ጉባኤው በሰጠው መግለጫ አስገንዝቧል፡፡

 

በመሆኑም የተሠራው ፊልም በማንኛውም አጋጣሚ ለዕይታ ቢቀርብ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የማታውቀውና የማትቀበለው መሆኑን ምእመናን ተገንዝበው ሕዝበ ክርስቲያኑ ራሳቸውን ከስሕተት እንዲጠብቁ የሊቃውንት ጉባኤው ጥሪውን አስተላልፏል፡፡

ቅርሶችን በተመለከተ ዐውደ ጥናት ተካሔደ

ኅዳር 22/2004 ዓ.ም

በእንዳለ ደምስስ

የማይዳሰሱ ባሕላዊ ቅርሶች አያያዝ /አተገባበር/ ስምምነት በሀገር አቀፍ ደረጃ /Implementation of the Intangible cultural Heritage convention at national level/ በሚል ርዕስ ዐውደ ጥናት ተካሔደ፡፡ ዐውደ ጥናቱ የባሕልና ቱሪዝም ሚኒስቴር የቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለስልጣን ከተባበሩት መንግሥታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ተቋም /UNESCO/ ጋር በመተባበር ያዘጋጀው ሲሆን፤ ከኅዳር 4-8/2004 ዓ.ም ድረስ ለአምስት ተከታታይ ቀናት ለመካሔድ ችሏል፡፡ በዐውደ ጥናቱ ላይ የዩኒስኮ ተወካይ በሆኑት በፕሮፌሰር አማርሰዋር ጋላ እና በቅርስና ጥበቃ ባለስልጣን ባለሙያዎች ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበው ሰፊ ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡

በዐውደ ጥናቱ ላይ የየክልሉ የቅርስና ጥበቃ መሥሪያ ቤት ተወካዮችና ባለሙያዎች የማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማእከልና የሚመለከታቸው አካላት የተገኙ ሲሆን፤ በሀገራችን ውስጥ የሚገኙ የማይዳሰሱ /Intangible/ ቅርሶችን ኅብረተሰቡ እንዲያውቃቸው እንዲጠብቃቸው፣ እንዲያስተዋውቃቸውና በዓለም ቅርስነት እንዲያስመዘግባቸው ከዓለም አቀፍ የቅርስና ጥበቃ ስምምነት ጋር በተጣጣመ መልኩ ለማራመድ እንዲቻል ግንዛቤ ለማስጨበጥ ታስቦ የተዘጋጀ ነው፡፡ የሌሎች ሀገራት ተሞክሮዎች በዐውደ ጥናቱ ላይ በሰፊው ተዳሰዋል፡፡

 

ዐውደ ጥናቱ ያተኮረባቸው መሠረታዊ ነጥቦችን ስንመለከት፣ ጥበቃ የሚያስፈልጋቸው የማይዳሰሱ /intangible/ ባሕላዊና ሃይማኖታዊ ቅርሶችን በተለይም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የምትጠቀምበትን የቅዳሴ፣ የያሬድ ዜማዎች፣ የአቋቋም፣ የቅኔ፣ እንዲሁም ሌሎች የብሔር ብሔረሰቦች ባህላዊ እሴቶቻችንን ለማየት ተሞክሯል፡፡ ለትውልድ ለማስተላለፍ በሀገር አቀፍ ደረጃ ማን ምን ያድርግ? ለሚለው ጥያቄ ማኅበረሰቡ፣ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች፣ ባለሙያዎችና የጥናትና ምርምር ተቋማት እንዲሁም ግለሰቦች ማከናወን ስለሚገባቸው ተግባራት በስፋት የተዳሰሱ ጉዳዮች ናቸው፡፡ በተጨማሪም የማይዳሰሱ በተሰኙ ቅርሶች ዙሪያ ለሚመለከታቸው አካላት ግንዛቤ ለማስጨበጥ መከናወን ስለሚገባቸው ተግባራት ለይቶ ማውጣትና መለካት፣ ማኅበረሰቡን ማሳተፍ፣ ቀጣይነት ያለው ጥበቃና ክትትል ማድረግ እንደሚያስፈልግ በጥናቱ ተጠቁሟል፡፡

የማይዳሰሱ /Intangible/ የሆኑ ሃይማኖታዊና ባህላዊ ቅርሶችን በተመለከተ የወጡ ፖሊሲዎችንና አዋጆችን ተግባራዊ ማድረግ፣ ጥናትና ጥበቃ የሚደረግላቸውን ቅርሶች ለመንከባከብ እንዲቻል የተለያዩ ተደራሽ አካላትን መምረጥ፣ ማደራጀትና ማዋቀር፣ ከዓለም አቀፍ ተቋማት ጋር በጋራ በመሥራት ድጋፎችን ማግኘት የሚቻልበት መንገድ ማመቻቸት እንደማገባ ተገልጿል፡፡

ዐውደ ጥናቱ በባህልና ቱሪዝም የቅርስ ጥበቃ ባለሙያዎችንና ሌሎች ባለድርሻ አካላትን ያካተተ እንደመሆኑ በቡድን በቡድን በመሆን አሉ የተባሉ ጠቃሚና ጎጂ ተጽዕኖዎች በማይዳሰሱ ሃይማኖታዊና ባህላዊ ቅርሶች ዙሪያ /positive and negative impacts to Implement Intangible cultural heritage/ በዝርዝር ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡

በዐውደ ጥናቱም ከተለያዩ የቅርስና ጥበቃ ባለሙያዎች ጥናቶች ቀርበዋል፡፡ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የጥናትና ምርምር ማዕከል የተለያዩ ተሞክሮዎችን ለታዳሚው ማካፈል የተቻለ ሲሆን በቀጣይነትም በጋራ ለመሥራት የሚያስችሉ በጎ ገጽታዎችን ለመፍጠር ጥረት ተደርጓል፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ያሏትን የማይዳሰሱ /Intangible/ ቅርሶች ሃይማኖታዊና ባህላዊ እሴቶችን ለትውልድ ለማስተላለፍ የሚረዳና መንገዶችንም ያመቻቸ ዐውደ ጥናት በመሆኑ ከባለድርሻ አካላት ብዙ ይጠበቃል፡፡ ለአምስት ተከታታይ ቀናት የተካሔደው ዐውደ ጥናት ኅዳር 8/2004 ዓ.ም ተጠናቋል፡፡

የፍትሕ ነፃነትን የሚያስከብር የመንፈሳዊ ፍርድ ቤቶች ማጠናከሪያ ሕግ በቅዱስ ሲኖዶስ ጸደቀ


ኅዳር 22/2004
ዓ.ም

ዲ/ን አብርሃም አንዳርጌ
  • ረቂቅ ሕጉን የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንደሚያጸድቀው ይጠበቃል፡፡

የፍትሕ ነፃነትን የሚያስከብር የመንፈሳዊ ፍርድ ቤቶች ማጠናከሪያ ሕግን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በሙሉ ድምጽ ማጽደቁ ተገለጸ፡፡

ሕጉ የጸደቀው የሲኖዶሱ ምልዓተ ጉባኤ ጥቅምት 23 ቀን 2004 ዓ.ም ባደረገው ዓመታዊ የምልዓተ ጉባኤ ስብሰባ ላይ ሲሆን ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ፣ 30ኛውን ዓመታዊ አጠቃላይ ሰበካ ጉባኤ ሲከፍቱ በአስተላለፉት ቃለ በረከት “ውኃው ከአጠገባቸው እያለ ተጠምተው የሞቱ ብዙ ናቸው” ብለዋል፡፡ አያይዘውም የሕግ ምንጭ የሆነችው የኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች ፍትሕ ፍለጋ የዓለማዊውን ፍርድ ቤት ሲናፍቁና ሲያጨናንቁ ማየት ችግር መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ መፍትሔውም የዳኝነት ነፃነትን የሚያስከብረውን የሕግ ረቂቅ ለቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ  ማቅረብና  ማጽደቅ በመሆኑም ይህንኑ ማድረግ መቻሉም በማኅበረ ክርስቲያኑ ፍትሕን ለማስፈን የቆመ የመሠረት አለት ነው ብለዋል፡፡

የጠቅላይ ቤተ ክህነት ይግባኝ ሰሚ ፍርድ ቤት ዋና ሰብሳቢ መልአከ ምሕረት አምኃ መኳንንት በበኩላቸው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከዘመነ ሕገ ልቡና ጀምሮ የሕግ ምንጭ ሁና ለትውልድና ለሀገር ያበረከተችውን ሁለንተናዊ ሥርዓት የታሪክ መዛግብቱና ሊቃውንቱ የሚመሠክሩት እንደሆነ አስታውሰዋል፡፡ ይህንም መሥመር በመከተል የቤተ ክርስቲያኗን መንፈሳዊ ፍርድ ቤቶች እንደገና ለማቋቋምና ለማጠናከር በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና በሕግ ባለሙያዎች ተጠንቶ የተዘጋጀው ባለ 10 ገጽ የሕግ ረቂቅ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በኩል እውቅና አግኝቶ በሥራ ላይ እንዲውል ቅዱስ ሲኖዶስ የሕጉን ረቂቅ በሙሉ ድምጽ ማጽደቁን ጨምረው አስታውቀዋል፡፡

ሕጉ የሚሰጣቸውን ጠቀሜታዎች አስመልክተው የጠቅላይ ቤተ ክህነት ይግባኝ ሰሚ ፍርድ ቤት ዋና ሰብሳቢ መልአከ ምሕረት አምኃ መኳንንት ጨምረው  እንዳስታወቁት ከጠቅላይ ቤተ ክህነት እስከ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን ባሉ አገልጋዮች፣ ሠራተኞችና በተቋማቱ መካከል ለሚነሡ ክርክሮች ሕጋዊ መፍትሔ መስጠቱ፤ እንዲሁም ከሞት በኋላ በውርስ ጊዜ በተለይ የመነኮሳትን ሀብት በመፈለግ ብቻ ሕጋዊ ባልሆነ ተዛምዶ /ዝምድና/ ሰበብ የቤተ ክርስቲያንን ክብር ለማስነቀፍ ከሚሞክሩ አካላት መከላከል ስለሚያስችልና በክርክር ጊዜ የተከራካሪዎችን ሃይማኖታዊ ክብር ማስጠበቁ በተጨማሪም በአሁኑ ጊዜ ከ500.000 በላይ የሚሆኑትን የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮችና ሠራተኞች መብትና ግዴታ በሕግ ለማስከበር ማገዙ የሚጠቀስ ሲሆን ቤተ ክርስቲያን በራሷ ፍርድ ቤት ፍትሕ ለማስፈን የምታደርገውን ጥረት እንደሚያግዝ ይጠቅማል ብለዋል፡፡

የዳኝነት ነፃነትን የሚያስከብረው የመንፈሳዊ ፍርድ ቤቶችን ማጠናከሪያ ሕግ እንዲጸድቅ ለሥራው መቃናት ዋናው ፈቃደ እግዚአብሔር ሆኖ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅና የኢሉባቦርና የጋምቤላ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ፊሊጶስ በሰጡት ቅን አመራር የሕጉ ረቂቅ በጠቅላይ ቤተ ክህነት አስተዳደር ጉባኤ ታይቶ በ30ኛው አጠቃላይ ሰበካ ጉባኤ ድጋፍ አግኝቶ ብፁዕነታቸው በሚመሩት ፍትሐዊ አመራር ተመቻችቶና ተዘጋጅቶ እንደቀረበ ለማወቅ ተችሏል፡፡

በስልጤና ሀድያ፣ ጉራጌ፣ ከንባታ ሀገረ ስብከት በፖሊሶች የፈረሰው የጋራሬ ቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያን በአክራሪ ሙስሊሞች ፍርስራሹ ተቃጠለ፡፡

ኅዳር 21/2004 ዓ.ም

በዲ/ን ኅሩይ ባዬ

፠በቃጠሎው ወንጀል የስልጤ ቲትጎራ 1ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት እና የስልጢ 2ኛ ደረጃ ተማሪዎች ተሳትፍበውታል፡፡
፠የስልጢ አረጋውያን ሙስሊሞች ድርጊቱን ተቃውመዋል፡፡

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በስልጤና ሀድያ፣ ጉራጌ፣ ከንባታ ሀገረ ስብከት በስልጤ ደብረ ስብሐት ቅድስት ማርያምና ቆቶ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ስር የተመሠረተው የጋራሬ ቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያን ኅዳር 19 ቀን 2004 ዓ.ም ረፋድ ላይ በአክራሪ ሙስሊሞች ሙሉ ለሙሉ መቃጠሉን ለመረዳት ተችሏል፡፡

DSC01450

የቤተ ክርስቲያኑ መቃጠል እንደተሰማ የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስና የማኅበረ ቅዱሳን ልዑካን በቦታው ተገኝተዋል፡፡ ብፁዕነታቸው ወደ ስልጢ ከመሔዳቸው በፊት በቡታጅራ ከተማ ተገኝተው በቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን የማጽናኛ መልእክት በማስተላለፍ የቡታ ጅራ ሕዝበ ክርስቲያን እንዲረጋጋ አድርገዋል፡፡

ቤተ ክርስቲያኑ ለምንና እንዴት እንደተቃጠለ ለማጣራት የደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልላዊ መንግሥት የጸጥታ አስተዳዳር ምክትል ሓላፊ አቶ ኢዮብ አንበሳ፣ የክልሉ ርእሰ መስተዳድር አማካሪ አቶ ፋሲል ጌታቸውና የክልሉ የጸጥታ ዘርፍ የሥራ ሒደት ሓላፊ አቶ በረከት ጌኤ  ተገኝተዋል፡፡

ቤተ ክርስቲያኑ እንዲቃጠል ከፍተኛውን ድርሻ ወስደው ተማሪዎችን ሲቀሰቅሱ የነበሩ በስም የሚታወቁ ግለሰቦችና አክራሪ ሙስሊሞች እንደሆኑ ተገንዝበናል፡፡ የወረዳው አስተዳደር ጽ/ቤት ወንጀሉ እንዳይፈጸም የቅድሚያ ዝግጅት ለምን እንዳላደረገ ለቀረበለት ጥያቄ እንደ መንግሥት አስተዳደር በሃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ መግባት ስለሌለብን ነው የሚል ምላሽ ሰጥቷል፡፡ በሃይማኖት ጉዳይ የመንግሥት ጣልቃ ገብነት እስከ የት እንደሆነ በግልጽ ማብራራት ያልቻሉት የስልጤ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ሐያቱ ሙክታር “የተቃጠለው ቤተ ክርስቲያን አይደለም” የሚል ማስተባበያ ለመስጠት መሞከራቸውን አረጋግጠናል፡፡ ሆኖም የተቃጠለው ቤተ ክርስቲያን ለመሆኑ የፎቶግራፍ ማስረጃ ለክልሉ ባለስልጣናት ሊቀ ጳጳሱ አቅርበዋል፡፡ ዜጎች በሀገራቸው ተከባብረው፣ ተፈቃቅረው ለሰላም       ለልማትና ለእድገት በሚተጉበት በዚህ ወቅት መንግሥት ባለበት ከተማ እንዲህ ያለ ወንጀል መፈጸሙ ያሳዘናቸው ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ ወንጀሉን የፈጸሙ አካላትን ጉዳይ ለፍርድ የማቅረቡን ሒደት ከሚመለከታቸው የበላይ የመንግሥት አካላት ጋር በመወያየት ላይ መሆናቸውን አስታውቀዋል፡፡

ተማሪዎች ከትምህርት ገበታቸው ወጥተው ቤተ ክርስቲያንን ለማቃጠል ያነሣሣቸውን አካል በሕግ መጠየቅ እንዳለበት ያብራሩት የክልሉ የጸጥታ አስተዳዳሪም የሕዝበ ክርስቲያኑን ትእግሥት አድንቀዋል፡፡

ኅዳር 19 ቀን 2004 ዓ.ም አመሻሽ ላይ የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ፣ የስልጢ ከተማ ምእመናንና የክልሉ የመንግሥት ባለሥልጣናት በተገኙበት ከ25 እስከ 30 የሚሆኑ የምእመናን ተወካዮች ተመርጠው ከሚመለከታቸው የሕግ አካላት ጋር ወንጀለኞችን ለማጋለጥ የማጣራቱ ሒደት ቀጥሏል፡፡

ዛሬ በደረሰን መረጃ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስና የመንግሥት ባለሥልጣናት በተገኙበት በምእመናን የተመረጡ ከ25 እስከ 30 የሚሆኑ ሽማግሌዎች ሥራቸውን እንዳይጀምሩ እየተደረገ ነው፡፡ በተለይ ከ1938 ዓ.ም ጀምሮ የደብረ ስብሐት ቅድስት ማርያምና ቆቶ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ለጥምቀተ ባሕር የሚጠቀሙበት ቦታ ለሌላ አገልግሎት መዋል የለበትም የሚል አቤቱታ ሲያቀርቡ የነበሩ ካህናት በኮሚቴ ውስጥ ቢመረጡም ሥራቸውን መቀጠል አልቻሉም፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ጉዳዩን በደንብ የማያውቁት ሰዎች እንዲተኩ መደረጋቸው የችግሩን መንስኤና ዘለቄታዊ መፍትሔ ለማግኘት አጠራጣሪ እንደሆነ የአካባቢው ምእመናን ጠቁመዋል፡፡

 

ኅዳር 19 ቀን 2004 ዓ.ም የቤተ ክርስቲያኑን መፍረስ የዘገብን መሆኑ ይታወቃል፡፡ የቃጠሎውን ተግባር የፈጸሙት በእድሜ ያልበሰሉ ሕፃናት ናቸው ተብሎ ወንጀሉ እንዲዳፈን መደረጉ እንዳሳዘናቸው የስልጢ ምእመናን እያሳሰቡ ነው፡፡

በስልጤና ሀድያ ጉራጌ ሀገረ ስብከት የጋራሬ ቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያን በወረዳው ፓሊስ አባላት እንዲፈርስ መደረጉ ተገለጠ፡፡

ኅዳር 19/2004 ዓ.ም

በዲ/ን ኅሩይ ባዬ

•    ቤተ ክርስቲያኑ የፈረሰው እኩለ ሌሊት እንደሆነም ታውቋል፡፡
•    የስልጢ 2ኛ ከፍተኛ ደረጃ ተማሪዎች በቤተ ክርስቲያኑ መፍረስ እንዲተባበሩ እየተቀሰቀሱ ነው፡፡

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በስልጤና ሀድያ ሀገረ ስብከት በስልጤ የጋራሬ ቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያን ኅዳር 15 ቀን 2004 ዓ.ም ዓርብ ለቅዳሜ አጥቢያ እኩለ ሌሊት ላይ በወረዳው የፓሊስ አባላት የመፍረስ አደጋ እንደተጣለበት ከክልሉ የደረሰን ማስረጃ አረጋገጠ፡፡

በስልጤ ዞን በስልጢ ወረዳ በቆቶ ባለሦ ቀበሌ በቆቶ መንደር በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስም የይዞታ ቦታው በሰነድ እንዲረጋገጥ የደብሩ ሰበካ ጉባኤ ለደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልላዊ መንግሥት ለግብርና ገጠር ልማት ቢሮ ለተፈጥሮ ሀብትና የገጠር መሬት አስተዳደር ዘርፍ ባቀረበው ጥያቄ አግባብነት ያለው የመንግሥት የሥልጣን አካል በቀን 15/04/2003 ዓ.ም የይዞታ ማረጋገጫ ሰነዱን ለደብሩ ሰበካ ጉባኤ መስጠቱን መረጃዎች ያስረዳሉ፡፡

DSC00379

በተሰጠው የይዞታ ቦታ ተደጋጋሚ የሆነ ክስ ይቀርብ እንደነበር የሚገልጡት የወረዳው ምእመናን የተፈቀደው ቦታ ለጥምቀተ ባሕር በመሆን ማንኛውም የእምነት ተከታይ አምልኮውን ሊፈጽም እንደሚችል በተቃራኒ ወገን አቤቱታዎች መቅረባቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡ ሆኖም ከወረዳው ፍርድ ቤት እስከ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ድረስ ጉዳዩ በተደጋጋሚ ታይቶ የቤተ ክርስቲያኑ አገልግሎት በተፈቀደለት ቦታ መንፈሳዊ ሥራውን እንዲቀጥል በመዝገብ ቁጥር 05681 የተወሰነውን ውሳኔ በመጥቀስ የወረዳው ፍርድ ቤት በቀን 13/12/2003 ዓ.ም ከፍተኛ ፍርድ ቤቱ ደግሞ በቁጥር 16/507/23/205 በቀን 13/04/2003 ዓ.ም ባስተላለፈው ትእዛዝ አስታወቋል፡፡

የሕግ አግባብ ባለው መሥሪያ ቤት ተፈቅዶ መሠረቱ ተቀምጦ የተሠራው ቤተ ክርስቲያን ድንገት በመፍረሱ የተደናገጡት የስልጢ ምእመናን ጉዳዩን ለሚመለከተው የበላይ አካል ለማቅረብ ወደ ሐዋሳ አስተዳደር ጽ/ቤት በቀን 18/03/2004 ዓ.ም ጉዞአቸውን አቅንተዋል፡፡ በእለቱም የክልሉ የጸጥታና አስተዳደር ቢሮ የምእመናኑ አቤቱታ አግባብነት ያለው በመሆኑ አጣሪ ኃይል ወደ ቦታው እንደሚላክ ምላሽ እንደተሰጣቸው ተገልጧል፡፡

ኅዳር 19 ቀን 2004 ዓ.ም የደረሰን መረጃ እንደሚያመለክተው በስልጢ ከተማ ጥቂት አክራሪ ሙስሊሞች በሙስሊምና በክርስቲያኑ መካከል ግጭት እንዲፈጠር ቅስቀሳ እያደረጉ ነው፡፡ ከዚህም በተያያዘ በስልጢ ከተማ 1ኛ እና ከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት የሚማሩ ተማሪዎች ቤተ ክርስቲያኑ እንዲፈርስ የሚደረገውን ተግባር እንዲፈጽሙ መቀስቀሳቸውንና ተማሪዎቹ ተሰባስበው ወደ ቤተ ክርስቲያኑ በመሔድ ነዳጅ ጨምረው ቤተ ክርስቲያኑን ሙሉ በሙሉ ማቃጠላቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡

የስልጢ ምእመናን በሕግ ተፈቅዶ በተሰጣቸው ቦታ ቤተ ክርስቲያን ሠርተው መገልገል ሊጀምሩ በተዘጋጁበት ወቅት ሕጋዊ ነኝ በሚል የፖሊስ አካል በመንፈቀ ሌሊት እንዲፈርስ መደረጉና በሕገ ወጥ ወጣቶች እንዲቃጠል መደረጉ እንዳሳዘናቸው አብራርተዋል፡፡

ቀጣዩ ሒደት እንደደረሰን የምናሳውቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡

የሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት ያስገነባው ሕንፃ ተመረቀ

ዲ/ን ቴዎድሮስ ኃይሉ

•    የብፁዕ አቡነ ቄርሎስ 25ኛ ዓመት የብር እዩቤልዩ በዓልም ተያይዞ ተከብሯል

{gallery count=1 width=350 height=300 counter=1 links=0 alignment=center animation=3000}abunekerilos{/gallery}

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን የሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት ያስገነባው ባለ ሁለት ፎቅ ሁለገብ ሕንፃ፤ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ተወካዮች፣ የመንግሥት አመራር አካላት፣ የአድባራትና የገዳማት አስተዳዳሪዎች እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት ህዳር 10/2004 ዓ.ም የደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በብፁዕ አቡነ አትናቴዎስና በአቶ ሓየሎም ጣውዬ የወልድያ ከተማ ከንቲባ ተመረቀ፡፡

 

መልአከ ሐይል ስጦታው ሞላ በሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት የሰበካ ጉባኤ ማደራጃ ክፍል ኃላፊ  የአዳጎ ሕንፃ መሠራቱ ቤተ ክርስቲያኒቱ በስብከተ ወንጌል የምታደርገውን እንቅስቃሴ በጉልህ የሚደግፍ ነው ብለዋል ፡፡ የወልድያ ከተማ ከንቲባ አቶ ሓየሎም ጣውዬ በምረቃው ወቅት ‹‹ የሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት ሕዝቡን በእምነቱ የጸና፣ ሀገር ወዳድና በልማት ዋነኛ ተሳታፊ ለማድረግ እያከናወናቸው ያለው አበረታች የልማት ተግባራት መንግሥት ከያዛቸው የድኅነት ማስወገጃ ስትራቴጂዎች አንፃር የሚሄዱ ለመሆናቸው ምስክርነት የሚያሻው ጉዳይ አይደለም፡፡ ሀገረ ስብከቱ ከጀመራቸው የልማት ሥራዎች መካከል የወልድያ ከተማችን የኢንቬስትመንት እድገት የሚያሠራውን አዳጎ ላይ የተገነባው ሕንፃ ለሌሎችም አርአያ ከመሆን አልፎ ለብዙ ዜጎች የሥራ ዕድል ፈጥሮ ያለፈና አሁንም እየፈጠረ ያለነው ቢባል መጋነን አይሆንም ›› በማለት መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

 

ቦታው የሀገረ ስብከቱ ይዞታ በመሆኑ፣ በመሐል ከተማ ያለ ሆኖ ሕንፃው መገንባት ስላለበት እንዲሁም በመንግሥት አካላት በሕንፃ እንድትሰሩ እድሉ የእናንተ ነው ስለተባለ፤ ሕንፃውን ልንሠራ ችለናል በማለት መልአከ ሐይል ስጦታው ሞላ ተናግረዋል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን የሕንፃውን ፕላን በነጻ ሠርቶ መስጠቱ የሚያስመሰግነው ነው በማለትም አክለዋል ፡፡

 

ሀገረ ስብከቱ ያስገነባው አዳጎ ሕንፃ ባለሁለት ዘመናዊ ፎቅ ሲሆን ስድስት ሱቆች፤ አንድ ካፍቴሪያና ሬስቶራንት ፣ አንድ መለስተኛ አዳራሽ እና ሃያ ስድስት ለጽ/ቤት አገልግሎት የሚሰጡ ክፍሎች ያሉት ነው ፡፡ ሕንፃውን ለመሥራት ሁለት ዓመት የወሰደ ሲሆን በአጠቃላይም በ3.8 ሚሊዮን ብር ተጠናቋል፡፡

 

ከዚህ በፊት ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ ከበጎ አድራጊዎች ጠይቀው ባገኙት ከ300,000.00 ባላነሰ ወጪ የሀገረ ስብከቱ መንበረ ጵጵስና (ባለ አንድ ፎቅ ሕንፃ) እንዲሁም የካህናት ማሠልጠኛ በብር 260,000.00 መሠራቱ የሚታወስ ነው፡፡ ተያይዞም የብፁዕ አቡነ ቄርሎስ የሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ የቅዱስ ላሊበላ ደብር የበላይ ጠባቂና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል 25ኛ ዓመት የብር ኢዩቤልዩ በዓልም በደማቅ ሁኔታ ተከብሯል ፡፡

 

በሰሜን ወሎ ሀገረ ስበከት ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ ከመሾማቸው በፊት በወሎ ሀገረ ስብከት ሥር የነበረ መሆኑና ብፁዕነታቸው ከተሾሙ ጊዜ ጀምሮ ከህዳር ወር 1980 ዓ.ም ጀምሮ ከሀገረ ስብከቱ ባለመለየት በትጋት የወንጌል አገልግሎታቸውን እየተወጡ ያሉ አባት መሆናቸውን የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ መልአከ ገነት ዓለሙ አስማረ በወልድያ ከተማ ባህል አዳራሽ በተካሄደው ዝግጅት ተናግረዋል፡፡ ሥራ አስኪያጁ አያይዘው ብፁዕነታቸው ሊቀ ጳጳስ ሆነው ከተመደቡ ከ1980 ዓ.ም ጀምሮ ቀድሞ አንድ ብቻ የነበረውን ሰ/ት/ቤት አሁን ላይ አራት መቶ ሦስት መሆናቸውን ፣ አራት መቶ ሠላሳ አንድ  መምህራን መሰልጠናቸው፣ ከመቶ 20% ከብር 70,220.41 ወደ ብር 3,236,486.48 ማደጉን፣ በወረዳ ቤተ ክህነት ሠራተኞች ከሠላሳ አራት ወደ ሠባ ስድስት፣ ሀገረ ስብከቱ ሲመሰረት አምስት ሠራተኞች የነበሩ ሲሆን አሁን ሃያ ሁለት ሠራተኞች መጨመሩን፣ አጎራባች አህጉረ ስብከቶችን ሳይጨምር ለሀገረ ስብከቱ አገልጋዮች 7,618 የዲቁናና የቅስና ማዕረግ መስጠታቸውን፣ በምዕመናን ቁጥር በ173,791 ዕድገት መታየቱን፣ በወረዳ ደረጃ፣ በልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን በኩልና ሐዋርያዊ ጉዞ ያደረጉትን ግልጋሎት በሪፖርት አቅርበዋል፡፡

 

ከበዓሉ ታዳሚዎች ቅኔና መወድስ የቀረበ ሲሆን ምዕመናንም ለብፁዕነታቸው ረጅም የአገልግሎት ዕድሜን ከጤና ጋር እግዚአብሔር እንዲሰጣቸው ተመኝተዋል፡፡

 

ብፁዕነታቸው ያለባቸውን ከፍተኛ ሕመም በመቋቋም ለሠሩት ሥራም ከልዮ ልዮ አካላት ሽልማቶች የተበረከተላቸው ሲሆን የሀገረ ስብከቱ ሠራተኞችም ሙሉ መቀዳሻ አልባስ፣ ቆብና የእጅ መስቀል እንዲሁም ጥና ሲሸልሙ፤ የቅዱስ ላሊበላ ደብር በበኩሉ በትረ ሙሴ አበርክቶላቸዋል፡፡ ተያይዞም በአዳጎ ሕንፃ  አስተዋጽኦ ላደረጉ ልዩ ልዩ አካላት የሽልማትና የምስክር ወረቀት ተሰጥቷል፡፡

 

በዕለቱም የብፁዕነታቸውን ከልጅነታቸው ጀምሮ እስከአሁን ድረስ ያለውን ሐዋርያዊ አገልግሎት የያዘ መጽሔት ለንባብ በቅቷል፡፡

 

ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ በብፁዕ አቡነ ተክለ ሃይማኖት እጅ ግንቦት 30/1979 ዓ.ም የበዓለ መንፈስ ቅዱስ ዕለት ከአምስት አባቶች ጋር ለጵጵስ  ሹመት የበቁ ሲሆን እንደተሾሙም የተመደቡት በሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት መሆኑ ይታወቃል፡፡ ብፁነታቸው በሰሜን ወሎና ዋግ ኽምራ አሁጉረ ሰብከት በዋናነት ያገለገሉና እያገለገሉ ያሉ ሲሆን በተጨማሪም የአሰብ፣ የደቡብ ወሎ እና የደቡብ ሸዋ ሀገረ ስብከትን በሊቀ ጵጵስና ደርበው እንዲሁም በ1986 ዓመተ ምሕረት በምሥራቅ ሸዋ ተዛውረው ለስምንት ወራት አገልግለዋል ፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ከአዲሱ የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሓላፊ ጋር ስለ ቀጣዩ የአገልግሎት ዘመን ተወያየ፡፡

ኅዳር 8/2004 ዓ.ም

በዲ/ን ኅሩይ ባየ

ማኅበረ ቅዱሳን ከአዲሱ የሰ/ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሓላፊ መልአከ ጽዮን ቆሞስ አባ ኅሩይ ጋር ኅዳር 7 ቀን 2004 ዓ.ም ስለ ቀጣዩ የአገልግሎት ዘመን ተወያየ፡፡
በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት በሰ/ት/ቤቶች ማደሪጃ መምሪያ ቢሮ በተደረገው ውይይት፣ ማኅበረ ቅዱሳን ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል የተነሣባቸውን ወደ ዐሥራ ሁለት የሚሆኑ ነጥቦችን በማብራራት የማኅበሩ ሰብሳቢ ሊቀ ትጉሃን ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ስዩም ንግግር ያደረጉ ሲሆን ለአዲሱ የመምሪያ ሓላፊ የማኅበሩን አጠቃላይ አሠራር በተሰጠው ሕግና መመሪያ መሠረት እንዲቆጣጠሩና በቅርብ እንዲከታተሉ ጨምረው ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡
Aba Heruye
መልአከ ጽዮን አባ ኅሩይም ከዐሥራ ሁለት ዓመት የውጭ ሀገር አገልግሎት በኋላ በፈቃደ እግዚአብሔር በቅዱስ ፖትርያርኩና በብፁዓን አባቶች ይሁንታ እንዲያገለግሉ ሲጠሩ ደስታ እንደተሰማቸው በመግለጥ፣ “የሰው ልጆች ጠባይ እንደ መልካችን የተለያየ ቢሆንም እንደ አመላችን ሰብስባ የያዘችን ቤተ ክርስቲያን ናት፣ የቤተ ክርስቲያናችን የአሠራር መንገዱ አንድ ነው፤ ስለዚህ የተገናኘነው በቤተ ክርስቲያንና ስለ ቤተ ክርስቲያን ስለሆነ በአባቶቻችን ጸሎት እየታገዝን እናገለግላለን” ብለዋል፡፡
በውይይቱ ላይ የተገኙት የከምባታ፣ ሀድያና ስልጤና ጉራጌ አህጉረ ስብከት እንዲሁም የሰ/ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ እንዳስታወቁት ማኅበረ ቅዱሳን ራሱን ደሴት አድርጎ ለብቻው የሚጓዝ ተቋም ሳይሆን በቤተ ክርስቲያን መዋቅር ውስጥ ያለ ማኅበር ነው፡፡ በመሆኑም በመደማመጥ እና በመወያየት ከሠራን ችግር አይኖርም፡፡ መለያየት ለጠላት ያመቻል፡፡ አንድ ከሆንን ግን ልዩነታችንን የሚፈልጉ ሰዎች መግቢያ አይኖራቸውም፤ ስለዚህ ለመልካም ነገር በሮቻችንን እየከፈትን ለመጥፎ ነገር ደጃችንን ልንዘጋ ይገባል ብለው፣ የምንሠራው ሥራ ውጤታማ የሚሆነው በመፈቃቀር፣ በመቀራረብ፣ በመወያየትና የቤተ ክርስቲያንን መዋቅር ጠብቀን ስንሠራ ነው በማለት አሳስበዋል፡፡
ብፁዕነታቸው አያይዘው መልአከ ጽዮን አባ ኅሩይን የተሰጣቸውን ትልቅ ሓላፊነት በእውነትና በሐቅ እንዲወጡ አባታዊ ምክር አስተላልፈዋል፡፡
በውይይቱ የማደራጃ መምሪያው ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ፣ የማደራጃ መምሪያው ኃላፊ መልአከ ጽዮን አባ ኅሩይ መሸሻ፣ የማኅበረ ቅዱሳን ሥራ አመራር ጉባኤ፣ ሥራ አስፈጻሚ፣ ኦዲትና ኢንስፔክሽን፣ የኢዲቶሪያል ቦርድ አባላትና የሚዲያ ክፍል አገልጋዮች እንዲሁም ልዩ ልዩ የማኅበሩ አባላት ተገኝተዋል፡፡
መልአከ ጽዮን አባ ኅሩይ ከሰ/ት/ቤት ወጣቶችና በሥራቸው ካሉ ማኅበራት ጋር ተግባብተው እና ተናበው አገልግሎታቸውን እንደሚወጡ ይጠበቃል፡፡