አሻራ አዲስ መንፈሳዊ ተውኔት

አዲስ መንፈሳዊ ተውኔት ይመረቃል

በይበልጣል ሙላት

ሰኔ 6፣2003ዓ.ም

በማኅበረ ቅዱሳን የአዲስ አበባ ማዕከል የትምህርትና ኪነጥበባት ክፍል የተዘጋጀውና “አሻራ” የሚል ስያሜ የያዘው ተውኔት ይመረቃል፡፡

ተውኔቱ እሑድ ሰኔ 12 ቀን 2003 ዓ.ም ከቀኑ 8፡00 በማኅበረ ቅዱሳን ህንፃ እንደሚመረቅ የተገለጸ ሲሆን ከዚያ በኋላ ለምዕመናን ክፍት ይሆናል ተብሏል፡፡

  አሻራ አዲስ መንፈሳዊ ተውኔት
የተውኔቱ አስተባባሪ አቶ አበራ ምታው ስብከተ ወንጌል በተለያየ ዘዴና መልክ እንደሚተላለፍ ገልጸው የሰዎችን ቀልብ ስቦ በመያዘ በቀላሉና በማይረሳ መልኩ ለማስተማርና ሃይማኖታዊ መነቃቃትንም ለመፍጠር እንደሚጠቅም አስገንዝበዋል፡፡

ተውኔቱ ሕዝበ ክርስቲያኑ ቅርሱን እንዴት? ከማን? እና መቼ? መጠበቅ እንዳለበት እንዲሁም እስከምን ድረስ መስዋዕትነት መክፈል እንዳለበት የሚያስገነዝብ ሲሆን ስለ ሃይማኖት ጽናትና ስለመንፈሳዊ ጥበብም እንደሚያስተምር አያይዘው ዓላማውን ገልጸዋል፡፡

በተውኔቱ 12 ሰዎች የተሳተፉ ሲሆን ለማዘጋጀትም ከአንድ ዓመት ጊዜ በላይ ፈጅቷል፡፡ በዝግጅት ወቅት የተለያዩ ችግሮችን እንዳለፉ የገለጹት አቶ አበራ በተለይ የመለማመጃ ቦታ አለመመቸት፣ የበጀት በጊዜው አለመድረስና የተዋንያኑ የሥራ መደራረብ ችግር እንደፈጠረባቸው አልሸሸጉም፡፡

ይህ ተውኔት ሕዝበ ክርስቲያኑ በዚህ መንገድ ስብከተ ወንጌልን ማስፋፋት እንደሚቻል ለማስገንዘብ የበኩሉን ድርሻ እንደሚወጣና ደራስያን ተዋንያንና ሌሎች የኪነጥበብ ባለሙያዎች ከዚህ ዘርፍ በመሳተፍ ክርስቲያናዊ ግዴታቸውን እንዲወጡ ያበረታታል ሲሉ አቶ አበራ ያሳስባሉ፡፡

በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ አባቶችና ጥሪ የተደረገላቸው ምዕመናን እንደሚገኙ ይጠበቃል፡፡

 

Debub_Omo1.jpg

በኦሞ ወንዞች ዙሪያ ተስፋ የሚያደርጉ ዓይኖች!

በማኅደረ ታሪኩና ተ/ሥላሴ ጸጋ ኪሮስ
ሰኔ 03፣ 2003 ዓ.ም 
 

Debub_Omo1.jpg

 
ከሐመር ብሔረሰብ አባላት ለአንዱ፣ የፈጠራችሁ ማን ነው? ብላችሁ ጥያቄ ብታቀርቡ በእምነት በጠጠረ፣ ጥያቄያዊ በሆነ ፊትና የዋሕ ልቡና “ቦርጆ ነዋ! ቦርጆ፣ ከእርሱ በረከት ያልተቋደሰ፣ በእርሱ እቅፍ ውስጥ የሌለ፣ እርሱ ያላበላው፣ እርሱ ያላጠጣው ማን አለ? እርሱ ሁሉን በፍቅር የሚንከባከብ፣ ሕፃናትን የሚያሳድግ የፍቅር አምላክ ነው” ይሏችኋል፡፡

በዚህም አያቆሙም “ቦርጆ በእኛ መካከል ሲኖር ነበር፣ በቆይታ አንዳንዶችDebub_Omo22.jpg በልባቸው ክፉ አስበው አስቀየሙት፣ ቦርጆን ገረፉት፣ መቱት፣ አቆሰሉት፡፡ እርሱም ከእንግዲህ ‘ከእናንተ ጋር ሆኜ /እየኖርኩ/ የማበላችሁ የማጠጣችሁ አይምሰላችሁ፡፡ ወደ ሰማይ እሄዳለሁ በልባችሁ ግን ለምኑኝ አበላችኋለሁ፣ አጠጣችኋለሁ’ ብሎን ሄዷል፡፡” በማለት ስለ አምላካቸው ያብራራሉ፡፡

 
ብዙ ጥናት የሚጠይቅ ጉዳይ ቢሆንም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ይገልጻል፡፡ የደቡብ ኢትዮጵያን ክፍል አቡነ ተክለሃይማኖት፣ አቡነ ዜና ማርቆስ እና ሌሎችም ቅዱሳን አበው የደከሙበት፣ የወንጌልን የምሥራች፤ የጌታችንን በዚህ ዓለም ከእኛ ጋር ተመላልሶ ማስተማሩን፣ አበርክቶ ማብላቱን፣ ተአምራት ማድረጉን፣ መገረፉን፣ መሰቃየቱን፣ መሰቀሉን፣ መሞቱን፣ መነሣቱን፣ ማረጉን ያስተማሩበት፣ ያመኑትንም ያጠመቁበት፣ በኪደተ እግራቸው የባረኩት ምድር ነው፡፡ ማን ያውቃል ይሄ የቦርጆ ትርክት ከዚያ መጥቶ ቢሆንስ? ለአሁኑ እግረ መንገዳችንን አንሣነው እንጂ ጉዳያችን ይሄ ሆኖ አይደለም፡፡ በደቡብ ኦሞ ሀገረ ስብከት እየተሠራ ያለውን ስብከተ ወንጌል የማስፋፋት አቢይ ተግባርና ተያያዥ ጉዳዮችን በአጭሩ ለመቃኘት እንጂ፡፡
 
ሀገረ ስብከቱ
ከአዲስ አበባ 781 ኪ.ሜ. ርቀት ላይ መቀመጫውን ጂንካ ከተማ ያደረገው የደቡብ ኦሞ ሀገረ ስብከት በሥሩ ዘጠኝ ወረዳዎች ያሉት ሲሆን በእነዚህ ወረዳዎች እስከ 1998 ዓ.ም 29 አብያተ ክርስቲያናት ታንጸው ነበር፡፡
በዞኑ 440.623 የሚጠጋ ሕዝብ ያለ ሲሆን ከእነዚህም 24.35 በመቶው የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታዮች ቀሪዎችም የባዕድ አምልኮ የተወሰኑትም የሌሎች እምነት ተከታዮች ናቸው፡፡
ከ16 ያላነሱ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ይገኛሉ፡፡ ከእነዚህም ሐመር፤ በና፤ ፀማይ፤ ካሮ፤ ዲሚ፤ ባጫ፣ ዳሰነች፣ ኤርቦሬ፣ ማሊ፣ አሪ፣ በዲ፣ ሙርሲና የመሳሰሉት ይገኙበታል፡፡

ዋላ ወደ ውሃ ምንጭ እንደሚናፍቅ ነፈሴ ወደ ሕያው አምላክ ተጠማች፡፡

በሀገረ ስብከቱ የሚገኙት አብያተ ክርስቲያናት የታነፁት ከተማን መሠረትDebub_Omo15.jpg አድርገው በመሆኑ ከ90 በመቶ በላይ የሚሆነውን የገጠራማ ቀበሌዎች ሕዝብ ያገናዘበ አልነበረም፡፡ ስለዚህም የገጠሩ ሕዝብ መጠመቅ እያማረው ሳይጠመቅ፣ መማር እያማረው ሳይማር፣ መስቀሉን መሳለም እያማረው ሳይሳለም፤ ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ “ዋላ ወደ ውሃ ምንጭ እንደሚናፍቅ ነፍሴ ወደ ሕያው አምላክ ተጠማች” እንዳለው ነፍሳቸው አምላክን እንደናፈቀችና እንደተጠማች ብዙ ቀኖች መሽተው ብዙ ሌሊቶች ነግተዋል፡፡ መዝ 41፥1

አንድ የአካባቢው ምእመን ‹‹ከእንግዲህ ብሞትም አይቆጨኝ፤ ሥጋዬ እንዲሁ በየሜዳው አይወድቅምና ይህ የዕድሜ ዘመኔ ሙሉ ናፍቆቴ ነበር” የሚለው ንግግራቸው የናፍቆታቸውን ልክ ያሳያል፡፡

Debub_Omo13.jpgየሀገረ ስብከቱ ሊቀጳጳስ ብፁዕ አቡነ ዕንባቆም በየቦታው በሚደርሱበት ጊዜ የሚኖረው አቀባበልና የሕዝቡ ስሜት፥ ለመጠመቅ ያለው ጉጉት ልዩ ነበር፡፡ አባታችን “ዝናብ አምጡልን የሚለው” የሽማግሌዎች ጥያቄ በፈጣሪ ያላቸውን ተአምኖ ያሳያል፡፡ አንድ አረጋዊ አባትም “እኛ እድላችን ሆኖ ታቦት በመምጣቱ እናመሰግናለን፡፡ አባታችንም በመምጣታቸው ደስ ብሎናል” በማለት በአስተርጓሚ ሲናገሩ በልዩ ስሜት ነበር፡፡

በቅርብ ጊዜ ሀገረ ስብከቱ ለሚያደርገው አብያተ ክርስቲያናትን የማነጽ፣ የመሠረት መስቀል የማስቀመጥ ሰፊ እንቅስቃሴ፥ ማኅበረሰቡ ሁሉ ርስቱ፣ ጉልቱ ማንነቱ የሆነውን መሬቱን በገዛ ፈቃዱ ነበር ቆርሶ የሰጠው፡፡ ይሄም የማኅበረሰቡን ለዚህች ቤተ ክርስቲያን ያለውን ፍቅርና ጉጉት አጉልቶ የሚያሳይ ታሪካዊ ክንዋኔ ነው፡፡

ከዚህም በላይ አንደኛው ሲጠመቅ ሌላኛው እኛስ መቼ ነው የምንጠመቀው? እያሉ ሀብተወልድና ስመ ክርስትና የሚያገኙበትን ቀን በመናፈቅ የሚያቀርቡት ጥያቄ ብፁዕነታቸው በደረሱበት ካህናትም በታዩበት ሁሉ የሚያጋጥም ነው፡፡

የቅዱስ ሲኖዶስ ትኩረትና የሀገረ ስብከቱ ምላሽ

እነዚህ ሕዝቦች ምንም እንኳን ክርስትናን ቢናፍቁም የተለያዩ ምክንያቶች ፍላጎታቸው እንዳይማላ እንቅፋት ተደርገው ሊጠቀሱ ይችላሉ፡፡ ሀገረ ስብከቱ በሰሜን ኦሞ ሀገረ ስብከት በሞግዚትነት መተዳደሩ አንደኛው ሲሆን ብሔረሰቦቹ ወደ ሰፈሩባቸው ቦታዎች ለመጓዝ በእግርና በበቅሎ እንጂ በተሽከርካሪ አስቸጋሪ መሆናቸው ይሄንንም ተቋቁሞ ለማስተማርና ለመቀደስ የሚችሉ በቂ ካህናት አለመኖራቸው እንደዋነኛ ምክንያት ይወሰዳሉ፡፡

ይሁንና ቅዱስ ሲኖዶስ ለቦታው በሰጠው ትኩረት ከ1998 ዓ.ም ወዲህ ሀገረ ስብከቱ ራሱን ችሎ መንበሩን ጅንካ ከተማ ላይ ተክሎ እንዲንቀሳቀስ ፈቅዶ ሊቀ ጳጳስ መድቦለታል፡፡

ሀገረ ስብከቱ ለውጦችን ለማምጣት እያደረገ ያለው እንቀስቃሴ የሚበረታታ እንደሆነ የተሠሩት ሥራዎች ያሳያሉ፡፡

Debub_Omo9.jpg90 በመቶ የሚሆነውን የሕብረተሰብ ክፍል ያማከሉ በተጨማሪ 37 ቦታዎች ላይ የመሠረት መስቀል ተቀምጧል፡፡ ወደፊት ቤተ ክርስቲያን እንደሚሠራባቸው ተስፋ ይደረጋል፡፡ ለጊዜው የአካባቢው ምእመናን በየዋሕ ልቡናና በፍጹም እምነት ቦታዎችን እየተሳለመ ይጠብቃቸዋል፡፡

እንደ ደራሽ ውሃ ድንገት አጥምቁን እያሉ በርካቶች እስከ አሁን እየመጡ ይገኛሉ፡፡ በዞኑ ከሚገኘት የተለያዩ የሕብረተሰብ ክፍሎች 50,000 የሚሆኑትን በማጥመቅ የሥላሴ ልጅነትን እንዲያገኙ የተደረገው ጥረት እጅግ የሚያበረታታ ነበር፡፡

ተባርከው የመስቀል ምልክት ከተደረገባቸው 37ቱ ቦታዎች የ16ቱ ግንባታDebub_Omo24.jpg ተጀምሯል፡፡ ከእነዚህም 6ቱ ለአገልግሎት ዝግጁ ሆነው በ3ቱ አገልግሎት መሥጠት ተጀምሯል፡፡  አማኞችን ለማብዛት፣ ያመኑትን ለማጽናት፣ ቀድሶ ለማቁረብ በቋንቋቸው የሚያስተምራቸው የአካባቢው ተወላጅ ያስፈልጋቸዋል፡፡ ከተጠመቁትም ካልተጠመቁትም የሕብረተሰብ ክፍሎች መካከል የአብነት ትምህርት እንዲማሩላቸው ፈቃደኛ የሆኑትን ልጆቻቸውን ሙሉ ወጪአቸውን በመሸፈን ጂንካ ከተማ በሚገኘው የአንቀጸ ብፁዓን አቡነ ተክለሃይማኖት ገዳም ገብተው እንዲማሩና የዲቁና ማዕረግ እንዲያገኙ ማድረግ ተችሏል፡፡ በዚህም ከወዲሁ አገልጋዮችን ለማግኘት የማስቻል ሥራን ያጠናክራል፡፡ ከዚህ ሁሉ የብፁዕ አቡነ ዕንባቆም ትጋትና ኖላዊ አባግዐነት ዋናውን ስፍራ የሚይዝ ነው፡፡

Debub_Omo27.jpgብፁዕነታቸው ከየብስ እስከ የባሕር ላይ ጉዞ፣ ከጂንካ እስከ ኬንያ ጠረፍ፣ ከእግር ጉዞ በሞተር ላይ ተፈናጥጦ እስከ መጓዝ ድረስ በ16ቱም የብሔረሰብ አባላት ዘንድ እየተገኙ ከደከመኝ ሰለቸኝ፣ ሕመም ተሰምቶኛልና ዛሬን ልረፍ፣ ዛሬ አይመቸኝም አልገኝም፣ ዙፋን ዘርጉልኝ ምንጣፍም አንጥፉልኝ ሳይሉ፣ እንደቀየው አብረው ተመግበው፣ ከሃገር ሽማግሌዎች ጋር በአንድ እቃ ቦርዴ ፉት በማለት ጠጥተው ማኅበረሰቡን መስለውና ተዋሕደው አፅናንተዋል፣ መክረዋል፣ አስተምረዋል፣ አጥምቀዋል፡፡ የሕፅናትን መዝሙር፣ የወጣቶችን ጭፈራ፣ የሽማግሌዎችን ምርቃት ተቀብለዋል፡፡
 
ቀሪ ተግባሮች

ይህ ሁሉ ሆኖ አሁንም ብፁዕነታቸውን የሚያሳስባቸው የአብያተ ክርስቲያናት መታነጽ፣ የማኅበረሰቡ በአንዲት ተዋሕዶ ጥላ ሥር መሰብሰብ ነው፡፡ “ከአሥራ ስድስቱም ወረዳዎች በርካታ ወገኖችን አጥምቀናል እያጠመቅንም ነው፡፡ በዝግጅት ላይ ያሉ እነዚህ ወገኖች ቤተ ክርስትያን ያስፈልጋቸዋል፣ ለወገን ደራሽ ወገን ስለሆነ በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ ያለን ለእነዚህ ወገኖች እንድረስላቸው፤ በሚያልፈውም ገንዘብ የማያልፈውን ርስት መንግሥተ ሰማያትን እንድንወርስ ጥሪዬን አስተላልፋለሁ” በማለት ያሳስባሉ፡፡

ቀደም ተብሎ እንደተገለጸው በርካታ ሥራዎች ቢሠሩም ገና የቀሩ ሥራዎች እንዳሉ መረዳት አያዳገትም፡፡ የሰው ሕንፃ መሠረት ተጣለ እንጅ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን የላቸውም፡፡ የብፁዕነታቸው ንግግርም ይሄንን ይገልጻል፡፡ የመሠረት መስቀል ከተቀመጠባቸው ቦታዎች 88 በመቶው የሚሆኑት አብያተ ክርስቲያናት ያልታነፁባቸው በመሆኑ ሕብረተሰቡ መስቀሎቹን በመሳለም የቀሪዎቹን ወገኖች መጠመቅ፣ የእነርሱን ዕለት ዕለት ሥጋ ወደሙ መቀበል፣ በቅፅረ ቤተ ክርስቲያን ጸሎት ማድረስን ተስፋ እያደረጉ ይገኛሉ፡፡

የሀገረ ስብከቱን አገልግሎት ከባድ አድርጎ የቆየው አንዱ ጉዳይ የሚሰጠው ትምህርተ ወንጌል በአስተርጓሚ መሠጠቱ ነው፡፡ ከየብሔረሱ ሰዎች አዲስ አበባ ድረስ አምጥቶ በማሰልጠን መልሶ ወደ አካባቢያቸው ማኅበረሰብ በመላክ ገብተው በቋንቋቸው እንዲያስተምሩ በማድረግ አጥጋቢ ውጤት ማግኘት ተችሏል፡፡ ይህ ሥራ በዋነኝነት ተጠናክሮ ሊቀጥል ይገባዋል፡፡ ለዚህም በጀት፣ አሠልጣኝ፣ የሥልጠና ቦታና ቁሳቁስ ያስፈልጋል፡፡ ይህም ከየትም አይመጣም፣ ከምእመናን እንጅ፡፡

በተለይም በእነዚህም በረሀማና ጠረፋማ በሆኑ አካሳቢዎች የወንጌል አልግሎት በዘላቂነት የሚዳሰስበትን መንገድ መቀየስ ያስፈልጋል፡፡

የሰማይ አምላክ ያከናውንልናል እኛ ባርያዎቹ ተነስተን እንሠራለን፡፡

የተጠቀሱት ችግሮች አጣዳፊ ምላሾችን የሚፈልጉ እንዲሁም በረጅም ጊዜ እቅድ የሚሠሩ ናቸው፡፡ አብዛኛዎቹም የምእመናንን ርብርብ የሚጠይቁ እንደሆነ ግልጽ ነው፡፡

Debub_Omo10.jpgይህንን ለማስተባበር የሚችል በሀገረ ስብከቱ ሊቀጳጳስ በብፁዕ አቡነ ዕንባቆም የሚመራ አንድ ዐቢይ ኮሚቴ ተቋቁሟል፡፡ “የደቡብ ኦሞ ሀገረ ስብከት ስብከተ ወንጌል ማስፋፊያልማትና ልማትና ሕንፃ ቤተ ክርስትያን አሠሪ ኮሚቴ” በሚል ስያሜ የተቋቋመው ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ ኢ/ር ዳንኤል ኃይለ “እኛ ተነስተናል የሰማዩ አምላክ ያከናውንልናል፡፡ ሕዝቡ ምኞቱ የመሠረት መስቀል የተሠራባቸውን ቦታዎች ቤተ ክርስቲያን ተሠርቶ ማየት ነው፡፡ ስለዚህ የመሠረት መስቀል የተተከለባቸው 37ቱ አብያተ ክርስትያናት እስኪሠሩ ድረስ፣ ስብከተ ወንጌል በአሥራ ስድስቱም ብሐሮች ቋንቋ እስኪሰበክ ድረስ እንተጋለን፡፡” የሚሉት ምክትል ሰብሳቢው ይቀጥሉና “ይህንን ለማድረግ የአጭር፣ የመካከለኛና የረጅም ጊዜ ስልታዊ ዕቅድ በመዘርጋት ከየብሔረሰቦች ዲያቆናትን፣ ካህናትን፣ መምህራንን አምጥቶ በማሰልጠን እናወጣለን ብለን እናስባለን፡፡ ይህንንም ከእግዚአብሔር ጋር እናሳካዋለን” ይላሉ፡፡

ለዚህ ሥራ እንዲያግዝ በማሰብ ኮሜቴው የሀገረ ስብከቱን እንቅስቃሴና የምእመኑን ሁኔታ የሚያሳይ አሳዛኝና ልብ የሚነካ ፊልም አዘጋጅቶ አቅርቧል፡፡ “በእውነት በዚህ ፊልም ሐዋርያዊ ተልዕኮ ምን እንደሚመስል ይረዱበታል” የሚለው ፊልሙን የተመለከተው ዲያቆን በረከት ነው፡፡ “ምን አልባትም ቀጣዮች ቅዱሳን ከዚያ አካባቢ ይመጡ ይሆናል፣ ማን ያውቃል?” በማለት ራሱን የሚጠይቀው ዲየቆን በረከት የምእመኑ ንፁህ እምነትና የዋህነት ልቡን የነካው ይመስላል፡፡

በዋነኝነት ግን ትኩረት ተሰጥቶ ለጊዜው የተሠራባቸውና እየተሠራባቸው ያሉ ዝግጅቶች አሉ፡፡ የመጀመሪያው ከግንቦት 24 እስከ 28/2003 ዓ.ም በቦሌ መድኃኒዓለም ቤተ ክርስቲያን ቅጽረ ግቢ ውስጥ የተዘጋጀው አውደ ርዕይ ነበር፡፡ በአውደ ርዕዩ የሀገረ ስብከቱ እንቅስቃሴዎች በሰፊው የተዳሰሱ ሲሆን ብዙ ምዕመናን ጎብኝተውታል፡፡ “እኔ ፕሮቴስታንት ነበርኩ፤ ከዛሬ ጀምሮ ግን ኦርቶዶክስ ሆኛለሁ፤ መጠመቅም እፈልጋለሁ” በማለት አንድ የፕሮቴስታንት እምነት ተከታይ አውደ ርዕዩን በማየት የተመለሰበት ሁኔታ ነበር፡፡  

እነዚህን ወገኖቻችን ለመታደግ ከተዘጋጁት መርሐ ግብራት ውስጥ በርካታ ምእመናን ይሳተፉበታል ተብሎ የሚጠበቀው ሰኔ 5 ቀን 2003 ዓ.ም በጠቅላይ ቤተ ክህነትና በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ አዳራሾች በተመሳሳይ ቀንና ሰዓት ይኸውም ከቀኑ 7፡00 ጀምሮ የሚደረገው ነው፡፡ ጉባኤው በአዲስ አበባ ከሚገኙ ሰ/ት/ቤቶች ኅብረት ጋር በጋራ የተዘጋጀ እንደሆነ ታውቁል፡፡

ይህ ጉባኤ የኢንተርኔትን ቴክኖሎጂ በመጠቀም በመላው ዓለም እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ሊሠራጭ የሚችልበት እድል እንደሚኖር አስተባባሪ ኮሜቴው ይገልጻል፡፡

የኢትዮጵያ ቤተ ክርስትያን ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ባለ እዳ ብትሆንም ገና ያላስተማረቻቸውና ያላጠመቀቻቸው በሥሯ ብዙ ምዕመናን አሉ፡፡ እነርሱም ሁሌ ጡት እንደሚፈልግ ሕፃን እጃቸውን ይልካሉ፣ እናቱ እንደጠፋችበት ሕፃን በር በሩን ይመለከታሉ፡፡ መቼ ይሆን የምንደርስላቸው? በእንደዚህ ዓይነት ጉባኤያት? ምን አልባትም አንዱ ሊሆን ይችላል፡፡

በማኅበረ ቅዱሳን የኅትመት ውጤቶች ላይ ተጥሎ የነበረው የአባ ሠረቀ ሕገ ወጥ ደብዳቤ ተሻረ

ተ/ሥላሴ ጸጋ ኪሮስ
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሓላፊ ቆሞስ አባ ሠረቀ ብርሃን ወልደ ሣሙኤል ማኅበረ ቅዱሳን የሚያሳትማቸው መጽሔትና ጋዜጣ ለኅትመት እንዳይውሉ የጻፉት ሕገ ወጥ የእግድ ደብዳቤ እንዲነሣ መደረጉን የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት አስታወቀ፡፡

በጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ፊርማ በቀን 01/10/2003 ዓ.ም ተጽፎ ለሚመለከታቸው አካላት የተሠራጨው ደብዳቤ እንዳመለከተው የማኅበረ ቅዱሳንና የመምሪያው ጉዳይ በወርኃ ግንቦት በተደረገው የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ላይ በአጀንዳነት ቀርቦ ችግሩን ለዘለቄታው ለመፍታት አጣሪ ኮሚቴ ተሰይሞ ባለበት ሁኔታ የመምሪያው ሓላፊ ሕገ ወጥ የእግድ ደብዳቤ መጻፉ አግባብ አይደለም ይላል፡፡

ማኅበሩ እገዳው አግባብ አለመሆኑን ለሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ ባቀረበው አቤቱታ ገልጿል።

ብፁዕነታቸው ለጠቅላይ ጽ/ቤቱ በቀን 29/09/2003 ዓ.ም በጻፉት ደብዳቤ «የመምሪያው ሓላፊ የማኅበሩ መጽሔትና ጋዜጣ ኅትመት ላይ እንዳይውሉ በማለት ለተለያዩ ማተሚያ ድርጅቶችና ብሮድካስት ባለሥልጣን መጻፉን አመልክቶ፥ የሰ/ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያና የማኅበረ ቅዱሳን ጉዳይ በአጀንዳነት ቀርቦ ችግሩን በዘለቄታው ለመፍታት ያስችል ዘንድ ጉዳዩን አጥንቶ የሚያቀርብ ከብፁዓን አበውና ከሊቃውንቱ የተውጣጡ አባላት ያሉት ኮሚቴ ተቋቁሞ ባለበት ወቅት ይህ የእግድ ደብዳቤ መጻፉ አስፈላጊ ነው ብዬ ባላምንም ከእኔ በላይ ሆኖ ስላገኘሁት ይህንኑ ጉዳይ ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ በትኩረት ተመልክቶ መፍትሔ እንዲሰጥበት» ማለታቸውን ተጠቅሷል፡፡

ይህንን የማደራጃ መምሪያውን የበላይ ሊቀ ጳጳስ ማሳሰቢያ ተከትሎም «የመጽሔትና ጋዜጣ ሕትመት እገዳው እንዲነሳ የተደረገ መሆኑን እናሳውቃለን» የሚለው የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ደብዳቤ ነው። በተጨማሪም በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሥር ስላለ የማኅበረ ቅዱሳን ሥራ እንቅስቃሴ ጉዳይ ተጣርቶ የሚያቀርብ ብፁዓን አባቶች ያሉበት ኮሚቴ ተሰይሞ ሥራውን ለመጀመር በዝግጅት ላይ ባለበት ወቅት ንትርክና ጭቅጭቅ መፈጠሩ የማጣራቱ ሥራ ሒደት ላይ እንቅፋት ሊፈጠር እንደሚችል ጠቁሟል፡፡

ይኸው የእገዳ ደብዳቤ እንደተነሣ ለብሮድካስት ባለሥልጣን እና ለሌሎች ስድስት ማተሚያ ቤቶች የተጻፈ ሲሆን ሌሎች የሚመለከታቸው አካላትም በግልባጭ እንዲደርሳቸው ተደርጓል፡፡

 
የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሓላፊ ቆሞስ አባ ሠረቀ ብርሃን ወልደ ሣሙኤል በጻፉት ተገቢ ያልሆነ የእገዳ ደብዳቤ ባለፈው ቅዳሜ ለኅትመት ገብታ የነበረችው 18ኛ ዓመት ቁጥር 18 ቅጽ 18 ቁጥር 226 /ከሰኔ 1 እስከ 15 ቀን 2003 ዓ.ም/ እትም ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ የኅትመት ጊዜዋ እንደተስተጓጎለ ታውቋል፡፡

ይሁንና ጋዜጣው በትናንትናው ዕለት ማለትም ግንቦት 30 ቀን 2003 ዓ.ም ለኅትመት በቅታ ምእመናን ዘንድ ደርሳለች፡፡

በቤተ ክርስቲያኗ መዋቅር ሥር ሆኖ በሚንቀሳቀሰው ማኅበረ ቅዱሳን አሳታሚነት ኅትመቷን ከጳጉሜን 5 ቀን 1985 ዓ.ም የጀመረችው ስምዐ ጽድቅ ለአንድም ዘመን ኅትመቷ ሳይስተጓጎል ምእመናንን ትምህርተ ሃይማኖትን በማስተማር፣ እምነትን በማጽናት፣ መናፍቃንንና አጽራረ ቤተ ክርስቲያንን በማጋለጥ፣ መንፈሳዊና ማኅበራዊ ጉዳዮችን በመዳሰስ ስታበረታና ስታጽናና እንደቆየች ይታወቃል፡፡ 

ለማስተጓጎል ተሞክሮ የነበረው የስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ እትም ስርጭት ላይ ዋለ።

ተ/ሥላሴ ጸጋ ኪሮስ
ለማተሚያ ድርጅቶች በተፃፈ አግባብነት የሌለውና መዋቅሩን ያልጠበቀ ደብዳቤ ለማስተጓጎል ተሞክሮ የነበረው የስምዐ ጽድቅ 18ኛ ዓመት ቁጥር 18 እትም ታትሞ መውጣቱ ተገለጸ። ህትመቱም ስርጭት ላይ ነው።

የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ኃላፊ አባ ሠረቀ ብርሃን ወልደ ሣሙኤል ለማተሚያ ቤቶች በፃፉት ደብዳቤ “የማኅበሩ መጽሔት ጋዜጣ በእናንተ በኩል ኅትመት ላይ እንዳይውሉ” በማለት ጠይቀው ነበር።

የማደራጃ መምሪያ የበላይ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ በበኩላቸው ይህ የማደራጃ መምሪያው ኃላፊ ደብዳቤ ህጋዊ እንዳልሆነ ለጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት በጻፉት ደብዳቤ አሳስበዋል። ይህንን ተከትሎ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ለማተሚያ ቤቶች የተፃፈውን አግባብነት የሌለው ደብዳቤ ለማንሣት ይጽፋሉ ተብሎ ይጠበቃል።

ማኅበሩ ያሉትን ሚዲያዎች በተመለከተ ከሚመለከታቸው የጠቅላይ ቤተ ክህነት አካላት ጋር ለመስራት ምክክር ከጀመረ ቆይቷል ሲሉ የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ ሊቀ ትጉሃን ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ስዩም ለአማርኛ መካነ ድር ገልጸዋል።

ቅዱስ ሲኖዶስ በግንቦቱ የርክበ ካህናት ምልዓተ ጉባኤ አጣሪ ኮሚቴ ሠይሞ የማኅበረ ቅዱሳንንና የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያን ጉዳይ ለማየት በወሰነበት ውቅት ይሄንን ደብዳቤ መጻፋቸው እንዲህም ለተለያዩ ሚዲያዎች መግለጫ መስጠታቸው ብዙዎችን ያነጋገረ ጉዳይ መሆኑ ይታወሳል።

 

capital C

Capital “C”

በድንቅነሽ ጸጋዬ

ሰኔ 1/2003 ዓ.ም.     

capital C

 
ዛሬ ደግሞ እንደ ሙአለ ሕፃናት ተማሪዎች Capital “C”ን እዚህ ምን አመጣት ትሉኝ ይሆናል፡፡ እኔም የትኩረት አቅጣጫዬ ስለ Capital “C” እንዳልሆነ እርግጠኛ ነኝ፡፡ ስለ ትምህርት ሲነሣ ወላጆቻችን ሀ ብለው የጀመሩት በተለምዶ ቄስ ትምህርት ቤት ብለን በምንጠራቸው ሲሆን፥ ትምህርቱም ይሰጥ የነበረው የሁሉም አፍ መፈቻ ቋንቋ ባይሆንም አብዛኛው ሰው ይግባበት በነበረው የአማርኛ ቋንቋ ፊደል ሀሁ፣ አቡጊዳ፣ መልዕክተ ዮሐንስ ዳዊት…ወዘተ፥ ዘመናዊውን የአስኳላ ትምህርት ከመቀጠላቸው በፊት፥ እንደተማሩ እናውቃለን፡፡ ለዚህም ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ዋነኛ የትምህርት ማዕከል ሆና አገልግላለች፡፡
ስማቸው በዓለም አቀፍ ደረጃ የገነነው የእንግሊዙ “ኦክስፎርድ” እና የአሜሪካው “ሃርቫርድ” ስመ ጥር ዩኒቨርሲቲዎች መነሻቸው ከቤተ ክርስቲያን ነበር፡፡ በዛሬው አኳኋን ተደራጅተውና በዘመናዊ ትምህርት ተውጠው ከመገኘታቸው በፊት የሃይማኖት ትምህርት ማሰልጠኛ ማዕከላት ነበሩ /የካቶሊክም ቢሆኑ/፡፡ ከዚህ የምንማረው ቁም ነገር፥ ዓለም ለደረሰበት የሥልጣኔ ቁንጮ የመድረስ ዋዜማውና መፍትሔው በሌሎች ላይ መንጠልጠል ሳይሆን በነባሩ /የራስ/ እሴት መሠረትነት ላይ ማነጹ እንደሆነ ነው፡፡ ለረጅም ዘመናት አገራችንን የመሩት ምሁራን ነገሥታቱና በየሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ የነበሩ ቁልፍ ሰዎች መገኛቸው የቤተ ክርስቲያን ትምህርት እንደነበርም አይካድም፡፡
 
የተለያዩ ጥናቶች እንደሚያመለክቱት፥ በየትኛውም አገር ተማሪዎች በአፍ መፍቻ ቋንቋቸው ሲማሩ ለትምህርት ያላቸው ፍላጎትና ተቀባይነት ብሎም የመረዳት ደረጃ ፈጣን ይሆናል፡፡ ከዚህም ባሻገር ለቋንቋው እድገትና ተተኪ ለማፍራት የሚያደርገው አስተዋጽኦ ቀላል አይሆንም፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስም ለአፍ መፍቻ ቋንቋ ትልቅ ቦታ ተሰጥቶት እናገኛዋለን፡፡ የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ወንጌል በመጀመሪያ የተጻፈው ወንጌላውያኑ እንደተሰማሩበት የስብከት ቋንቋ፥ ቅዱስ ማቴዎስ በምድረ ፍልስጥኤም በዕብራይስጥ፤ ቅዱስ ማርቆስ ለሮማውያን በሮማይስጥ፤ ቅዱስ ሉቃስ ለመቄዶንያ በጽርዕ እና ቅዱስ ዮሐንስ ለኤፌሶን በዮናናውያን ቋንቋዎች መሆኑን እንረዳለን፡፡
በተጨማሪም ሐዋ.2÷1 እንደምናገኘው ቅዱሳን ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስ በገለጠላቸው 72 ቋንቋዎች ከተለያየ ሀገር ለበዓል የተሰበሰቡትን ሕዝቦች በየሀገራቸው ቋንቋ ወንጌልን ስላስተማሯቸው በዕለቱ 3000 ሰዎች አምነው ተጠምቀዋል፡፡ ይህም ሰው በአፍ መፍቻ ቋንቋው ሲማር ለመረዳት እና ወደ ተግባር ለመለወጥ ፈጣን እንደሆነ ያረጋግጥልናል፡፡

ሐዋርያዊት እና ዓለም አቀፋዊት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንም ለአፍ መፍቻ ቋንቋ ትኩረት በመስጠት ሁሉም ወንጌልን ተምረው ከሥላሴ ልጅነትን አግኝተው መንግሥተ እግዚአብሔርን እንዲወርሱ ባላት አቅም በሁሉም አህጉረ ስብከቶች በመተግበር ላይ ትገኛለች፡፡ እኛስ ልጆቻችንን እንዴት እያስተማርናቸው ነው? በአፍ መፍቻ ቋንቋቸው? ቢያንስ ከሀገርኛ ቋንቋዎች በአንዱ? ወይስ ጥሩ እንግሊዝኛ ቋንቋ ተናጋሪ እንዲሁኑ ከማሰብ? አብዛኛው ባለሀብትም/የትምህርት ቤት ባለቤቶች/ የወላጆች አስተሳሰብ ስለገባቸው ደረጃውን ባይጠብቅም የትምህርት ቤቱ ስም በእንግሊዝኛ ሲሆን ኢንተርናሽናል የሚል ተጨምሮበት፣ ማስታወቂያቸው በውጭ ዜጋ መሆን ከጀመረ ሰንብቷል፡፡ ልክ ነዋ! በአገርኛ ቢጻፍ ማን ትኩረት ይሰጠዋል፡፡

ልጆቻችን በአፍ መፍቻቸው እየተማሩ ሌሎች የሀገራችንንም ሆነ የውጭ ቋንቋዎች ቢችሉ አይጠቅምም ባይ አይደለሁም፡፡ በአሁኑ ጊዜ እየሆነ ያለው ግን “የራስን ጥሎ” በአብዛኛው ትምህርት የሚጀምሩበት ቋንቋ እንግሊዘኛ መሆኑ ነው፡፡ ታዲያ ምን ችግር አለው የሚል አይጠፋም! ከአመታት በፊት የወንድሜን ልጆች ት/ቤት ልናደርስ እየሄድን የያዝኩትን መፍሔት ተቀብላ በፍጥነት Capital “C” አለችኝ፤ “ሐመር” ከሚለው ውስጥ “ር”ን ነጥላ በጣቷ እያመለከተችኝ፡፡ “ሐ” እና “መ”ን ግን እንደማታውቃቸው ስትገልጽልኝ በጣም ባዝንም አልፈረድኩባትም፡፡ A-for Apple, B-for Banana…. አየተባለች እንጂ በአፍ መፍቻዋ ፊደል እንድትቆጥር ከቤተሰብም ሆነ ከትምህርት ቤት እድል አላገኘችም፡፡ በአሁኑ ሰዓት የ7ኛ ክፍል ተማሪ ብትሆንም የአማርኛ ውጤቷ እንደሌላው ትምህርት የሚደነቅ አይደለም፡፡ ታናሽ ወንድሟም ቢሆን የዚሁ ችግር ተጠቂ ስለሆነ በጥናት ወቅት የአባቱን እርዳታ የሚጠይቀው የአፍ መፍቻ ቋንቋው ለሆነው ነገር ግን ብዙም ለማይረዳው ለአማርኛ ነው፡፡ አንድ ቀን ነው “አባቢ ሐረግ ምን ማለት ነው?” አለው፡፡ አባትም የቻለውን ያህል ገለጸለትና በደንብ የተረዳ ስላልመሰለው በእንግሊዘኛ “Phrase እንደማለት” ሲለው ፈገግ ብሎ “ነው እንዴ” አለ! ይገርማል አማርኛን ለማስረዳት በእንግሊዝኛ ተተርጉሞ ማለት ነው፡፡
ሌላ ልጨምርላችሁ በመዲናችን ውስጥ ካሉ ስመ ጥር ኢንተርናሽናል ትምህርት ቤቶች በአንዱ የ5ኛ ክፍል መምህርት ጓደኛ አለችኝ፡፡ ተምሮ መፈተን፥ አስተምሮ መፈተን ያለነውና አማርኛ ትምህርት ልትፈትን ወደ ክፍል ዘለቀች ከተማሪዎቹ አንዱ ፈተናውን ተቀብሎ ”ጀምሩ“ ሲባል “ሚስ አልፈተንም” ብሎ እርፍ፡፡ “ለምን?” ሚስ ጠየቀች “አስኪ ተመልከችው ስትራክቸሩ /የፊደሉ ቅርጽ/ ሲያስጠላ” አላት፡፡ በዚህ አቋሙ በመጽናቱ ሚስም ሳታነብ፣ እሱም ሳይፈተን ቀረላችሁ፡፡
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ “የአማርኛ ፊደላት በዝተዋልና ይቀነሱ” የሚሉ አስተየየቶች መነሣታቸውን አስታውሳለሁ፡፡ ዛሬ የፊደል ቅርጻቸው ያስጠላል ያሉን ሕፃናት ነገ ከነጭራሹ አያስፈልጉንም ላለማለታቸው ምን ያህል እርግጠኞች ነን? ቅኝ ብንገዛ ኖሮ እንግሊዝኛ እንችል ነበር ብለው በቁጭት የሚናገሩ ወገኖች እንዳሉም ባይዘነጋ፡፡ ይህን ሲሉ ግን ጣሊያን በኢትዮጵያ በነበረችባቸው አምስት ዓመታት ውስጥ አንድም ጣልያንኛ ቃል ያላወቁትን አስተውለዋል? አሁንስ ቢሆን በተዘዋዋሪ የአስተሳሰብ ቅኝ ተገዢዎች መሆናቸውንስ?
የዛሬ ሕፃናት የነገ ሀገር ተረካቢዎች መሆናቸው ለማንም ግልጽ ነው፡፡ የሀገራችን ባሕል ታሪክ እና የማንነታችን መገለጫ መዛግብቱ የተጻፉት ደግሞ በግዕዝ፣ በአማርኛ እና በሌሎች የብሔር ብሔረሰብ ቋንቋዎች መሆኑ ይታወቃል፡፡ ታዲያ ሕፃናቱ የሀገራቸውን ባሕል፣ ታሪክ ማንነት ለመረዳት በውጭ ቋንቋ ተተርጉሞ ካልመጣ ላያነቡ ነው? ስለ እኛ በውጭ ቋንቋዎች የተጻፉትስ ምን ያህል ሚዛናዊ ሆነው ማንነታችንን ይገልጻሉ?
በሀገር ውስጥ ካሉ ሕፃናት ይህን ከተመለከትን በውጭ የኑሮ ውጥረት በበዛበት ቤተሰብ ተከታትሎ ባሕላቸውን፣ ታሪካቸውን በአጠቃላይ ማንነታቸውን እየተነገሩ ያላደጉ ሕፃናት እንዴት ይሆኑ? ይህን ስል ግን ባላቸው የተጣበበ ሰዓት በየቤታቸው እና በየአብያተ ክርስቲያናቱ ፊደል የሚያሰቆጥሩ ባሕላቸውና ታሪካቸውን የሚያስተምሩ መኖራቸውን ሳልዘነጋ ነው፡፡
ሐሳቤን ለማጠቃለል ያህል ወላጆችስ ይህ ጉዳይ አሳስቦን ያውቃል? ወይስ ጥሩ የውጭ ቋንቋ ስለተናገሩልን በቃ የዕውቀት ዳር የደረሱልን መስሎን ዝም ብለን ተቀምጠናል? የሚረከቧትን ሀገር ታሪክ፣ ባሕልና ማንነት የማያቁ ተተኪዎች እያፈራን መሆናችንንስ አስበነው እናውቃለን? እኔ ግን “ር”ን Capital “C” ስትለኝ በሁኔታው አዝኜ ዝም ባልል ኖሮ “ዘ”ን ኤች፣ “ረ”ን ኤል፣ “ጠ”ን ስሞል ኤም፣ “ዐ”ን ኦ፣ “ተ”ን ስሞል ቲ፣ “ሀ”ን ዩ፣ “ሠ”ን ደብልዩ ወዘተ ልትለኝ እንደምትችል አልጠራጠርም፡፡

“አብዝቶ የመመገብ ጣጣው”

  (በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ)
ግንቦት 30/2003 ዓ.ም.

ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ

መግቢያ

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የዮሐንስን ወንጌል በተረጎመበት በ21ኛው ድርሳኑ “ ጌታችን በእናታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ጥያቄ በቃና ሰርግ ላይ ስለምን ውሃውን ወደ ወይን ጠጅነት እንደቀየረው  ከአብራራ በኋላ ከዛሬ 1500 ዓመት በፊት በአሁኑ ጊዜ እንደ አዲስ ግኝት ተደርገው የሚታዩትን አብዝቶ በመመገብ የሚመጡትን የጤና ጉድለቶች ጽፎልን እናገኛለን ፡፡ ጽሑፉ ተተርጉሞ እንዲህ ቀርቦአል።

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ውሃውን ወደ ወይን ጠጅነት ያኔ እንደቀየረ ዛሬም እኛን ድካማችንንና እንደ ወራጅ ውሃ በአንድ ቦታ ጸንቶ መቆየት የተሣነውን የሥጋ ፈቃዳችንን ከመቀየር አልተቆጠበም ፡፡ ዛሬም አዎን ዛሬም ልክ እንደ ወራጅ ውሃ ቀዝቃዛ ፣የፈጠነና ፣ ያልተረጋጋ ጠባይ ያላቸው ሰዎች አሉ ፡፡ እነዚህን ፈቃዶቻችንን ወደ ጌታችን እናምጣቸው ፤ እርሱ ወደ ወይንነት ይቀይራቸዋል፡፡ ከዚያም በኋላ ውኃ ሆነው ከእንግዲህ አይቀጥሉም ፡፡ ነገር ግን ለራሳቸውና ለሌሎች ደስታን የሚሰጡ አካላት ይሆናሉ ፡፡

ባልተረጋጋ ውሃ የተመሰሉት እነማን ናቸው ? ለዚህ ከንቱ ዓለም ሕሊናቸውን ያስገዙ ወገኖች ፣ የዚህን ዓለምን ቅምጥልነት ፣ አለቅነትንና ክብርን የሚሹ ናቸው፡፡ እነዚህ ፍቃዶቻችን እንደውኃ የሚፈሱ ፣ ፈጽሞ ያልተረጋጉ ፣ ለአመፃ የሚፋጠኑ ቁልቁል የሚምዘገዘጉ ውኆች ናቸው ፡፡
 
ዛሬ ሀብታም የነበረው ነገ ደሃ ይሆናል ፡፡ በአንድ ወቅት ዝናው ሲነገርለት፣ የተጌጠና የተንቆጠቆጠ ልብስ ለብሶ በሰረገላ ላይ የሚሄድና ብዙ አጃቢዎች የነበሩት ሰው ፣ ያለፈቃዱ ያን የተዋበ መኖሪያውን ተቀምቶ ወደ ወይኒ ተጥሎ ይገኛል ፡፡ ለሥጋው ደስታ የሚተጋው ሆዳሙ ደግሞ የሥጋ ፈቃዱን ከሞላ በኋላ ሆዱ ሳይጎድልበት ለአንድ ቀን መቆየት አይቻለውም ፡፡ ነገር ግን እነዚህ ምግቦች ከሆዱ ሲጠፉ ወደ ቀድሞው ምቾቱ ለመመለስ ሲል ከፊት ይልቅ አብዝቶ ይመገባል ፡፡ አመጋገቡም ሁሉን ጠራርጎ እንደሚበላ እንደጎርፍ ውሃ ነው ፡፡ በዝናብ ወቅት የሚነሣው ጎርፍ አስቀድሞ የነበረ ውሃ በከፈተለት ጎዳና ገብቶ ቦታውን ሁሉ ያጥለቀልቀዋል ፡፡ እንዲሁ በሆዳሙም ዘንድ እንዲህ ይሆናል ፡፡ አስቀድሞ የነበረው ሲጠፋ እርሱ በቀደደው ሌሎች  የሥጋ ፍቃዶች በዝተው ይገባሉ ፡፡
 
 ምድራዊው ነገር ይህን ይመስላል ፤ መቼም ቢሆን የተረጋጋ አይደለም ፡፡ መቼም ቢሆን አንዱ ሌላውን እየተካ የሚፈስ እና የሚቸኩል ነው ፡፡ ነገር ግን የቅምጥልነትን ኑሮ በተመለከተ ጣጣው በከንቱ መባከን ወይም መቻኮል ብቻ አይደለም ፡፡ ሌሎችም እኛን ከመከራ የሚጥሉን ችግሮችም አሉበት ፡፡ ቅምጥልነት ባመጣብን ጣጣ የሰውነት አቅማችን ይዳከማል ፣ እንዲሁም የነፍስ ጠባይዋም ይለወጣል ፡፡ ከባድ ጎርፍ ወንዙን በደለል ወዲያው እንደማይሞላው  ፣ ቀስ በቀስ ግን እንዲሞላው ፣ እንዲሁ ቅምጥልነትና ዋልጌነት እንደ አልማዝ ብርቱ የሆነውን ጤንነታችንን ቀስ በቀስ ውጦ ያጠፋዋል ፡፡
 
 ወደ ሐኪም ዘንድ ሄደህ ብትጠይቅ የበሽታዎች ሁሉ ምንጫቸው አብዝቶ ከመመገብ እንደሚመነጩ ይነግሩሃል ፡፡ ጠግቦ አለመብላትና ለሆድ የማይከብዱ ምግቦችን መመገብ ለጤንነት እናት ነው ፡፡ ስለዚህም የሕክምና ባለሙያዎች የጤንነት እናት ብለው ይጠሩታል ፡፡ እናም ጠግቦ አለመብላት የጤንነት እናት ከሆነ  ፣ አብዝቶ መመገብ ደግሞ የበሽታዎች ሁሉ እናት እንደሆነ በዚህ ይታወቃል፡፡ አብዝቶ መመገብ ሰውነታችንን አዳክሞ በሕክምና ባለሙያ እንኳ ለማይድን በሽታ አጋልጦ ይሰጠናል ፡፡
 
አብዝቶ መመገብ ለሪህ ፣ ለአእምሮ ውስጥ የደም መፍሰስ ፣ ለዐይን የማየት ኃይል መቀነስ ፣ ለእጅ መዛል ፣ ለአካል ልምሾነት  ፣ ለቆዳ መንጣት (ወደ ቢጫነት መቀየር  ፤ በተለምዶ የጉበት በሽታ ለምንለው ምልክት ነው ተብሎ ይታመናል ) ስጉና ድንጉጥ መሆን ፣ ለኃይለኛ ትኩሳት እና ከጠቀስናቸው በላይ ለሆኑ ሌሎች ሕመሞች ያጋልጣል ፡፡ በዚህ የሚመጡትን የጤንነት ጠንቆች በዚች ሰዓት ውስጥ ዘርዝሮ ለመጨረስ ጊዜው አይበቃም ፡፡ እነዚህ ሁሉ ሕመሞች በተፈጥሮአችን ላይ የሚከሰቱት መጥኖ በመብላት ወይም በጾም አይደለም ፡፡ ነገር ግን ከሆዳምነታችንና ከአልጠግብ ባይነታችን የተነሣ የሚመጡብን ናቸው ፡፡ በእነዚህ ምክንያቶች የተነሣ በነፍሳችን ላይ የሚከሰቱብንን  በሽታዎች ብንመለከት ዋዘኝነት ፣ ስንፍና ፣ ድንዛዜ ፣ የሥጋ ፍትወቶቻችን ማየል፣ እነዚህንና የመሳሰሉ ሕመሞች ነፍሳችንን ያጠቁዋታል ፡፡ ለእነዚህ ሁሉ ምንጫቸው ሳይመጥኑ አብዝቶ መመገብ ነው ፡፡ ከእንዲህ ዐይነት ቅጥ ያጣ አመጋገብ  በኋላ የቅምጥሎች ነፍስ ክፉ አውሬዎች ሥጋዋን ተቀራምተው ከተመገቡዋት አህያ ያልተሻለች ትሆናለች ፡፡ ቅምጥሎችን ስለሚጠብቃቸው  ሕመሞችና ስቃዮች ጨምሬ ልናገርን ? ከብዛታቸው የተነሣ ዘርዝሬ መጨረስ አይቻለኝም ፡፡
 ነገር ግን በአንድ ማጠቃለያ አሳብ ሁሉንም ግልጽ አድርጌ ማስረዳት እፈልጋለሁ ፡፡ እንዲህ ከሚያደርጉ ከቅምጥሎች ማዕድ ማንም ደስ ብሎት አይመገብ ፡፡ አስቀድመን እንደተነጋገርነው ጾምና መጥኖ መመገብ የደስታና የጤንነት ምንጮች ሲሆኑ ያለቅጥ መመገብ ግን የበሽታና የደስታ ማጣት ሥር እና ምንጭ ናቸውና ፡፡
ሁሉ ነገር ከተሟላልን ፍላጎት የለንም ፡፡ ፍላጎት ከሌለ ደግሞ እንዴት ደስታን ልናገኛት እንችላለን ? ስለዚህም ድሆች ከባለጠጎች ይልቅ የተሻለ ማስተዋልና ጤና ያላቸው ብቻ አይደሉም ፣ ነገር ግን ታላቅ በሆነ ደስታ ውስጥ የሚኖሩ ጭምር ናቸው ፡፡ ይህንን ከተረዳን ከመጠጥና ከቅምጥልነት ሕይወት ፈጥነን እንሽሽ ፣ ከማዕዱ ብቻ አይደለም ፣ ከዚህ ሕይወት ከሚገኙት ፍሬዎች ሁሉ እንሽሽ ፡፡  እነርሱን በመንፈሳዊ ሕይወት በሚገኘው ደስታ ለውጠን በቅድስና እንመላለስ  ፡፡ ነቢዩ “ በእግዚአብሔር ደስ ይበላችሁ እርሱ የልብህን  መሻት ይሰጥሃል”(መዝ.36፥4)  እንዳለው በጌታ ደስ ይበለን ፡፡ በዚህም ዓለም በሚመጣውም ዓለም በእርሱ በእግዚአብሔር መልካም ስጦታ ደስ ይለን ዘንድ የሰው ልጆችን በሚያፈቅረው በኩል ለእርሱ ለእግዚአብሔር አብ ለመንፈስ ቅዱስም ክብር ይሁን  እስከዘለዓለሙ ፡፡ አሜን !!          
   በነገራችን ላይ የሕክምና ባለሙያዎች እንዲሁም የፍልስፍና ምሁራን(ተማሪዎች) በዚህ በቅዱስ ዮሐንስ ገለጻ ላይ ምን ይላሉ ? በmkwebsitetechnique@gmail.com ጻፉልን።

በማ/ቅዱሳን የአሜሪካ ማዕከል ዓመታዊ ጠቅላላ ጉባኤ ውሳኔዎችን በማሳለፍ ተጠናቀቀ።

 
(የአሜሪካ ማዕከል፤ አትላንታ፤ ጆርጂያ)፦ “የቤተ ክርስቲያናችንን ህልውና መጠበቅ የሁላችንም ኃላፊነት ነው” በሚል መሪ ቃል ግንቦት 20, 21 እና 23/ 2003 ዓ.ም ሲካሔድ የቆየው በማ/ቅዱሳን የአሜሪካ ማዕከል ዓመታዊ ጠቅላላ ጉባኤ ውሳኔዎችን በማሳለፍ እና የ2004 ዓ.ምሕረትን ዕቅድ በማጽደቅ ተጠናቀቀ።

ለ13ኛ ጊዜ በተካሔደው እና የዲሲ እና አካባቢው ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ አብርሃም፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን አበው፣ ዲያቆናት ወንድሞች፣ የማኅበሩ አባላት ወንድሞች እና እህቶች እንዲሁም ተጋባዥ እንግዶች በተገኙበት የተካሔደው ጉባኤ የማዕከሉን የ2003 ዓ.ም ዓመታዊ የተግባር ድርጊቶች ሪፖርት ከማዳመጡም በላይ በቀረቡት ሪፖርቶች ላይ ውይይት አድርጓል። “የማዕከላችን የአገልግሎት ተግዳሮቶች እና የመፍትሔ አቅጣጫዎች”፣ “የማኅበሩ አባላት ማሕበራዊ ተሳትፎ” እንዲሁም “የቤተ ክርስቲያን አንድነት” በሚሉ ርእሶች ዙሪያ ትምህርቶች ተሰጥተው ውይይቶች ተደርጎባቸዋል።
 
ወደ ኢትዮጵያ ስለሚተላለፍ ሳምንታዊ የሬዲዮ ፕሮግራም ጉዳይ በሰፊው ተወያይቷል። የተዋሕዶ ድምጽ/ድምፀ ተዋሕዶ/ በመባል ስለተሰየመው እና በሳምንት ሁለት ቀን ወደ ኢትዮጵያ መተላለፍ ስለሚጀምረው የሬዲዮ ጣቢያ ጉዳዩ የሚመለከታቸው አባላት ያጠኑት ጥልቅ ጥናት ከቀረበ በኋላ ሰፊ ውይይት ተደርጎበታል።
ማኅበሩ ከዚህ በፊት ለአንድ ዓመት ያህል የሬዲዮ ዝግጅት በአጭር ሞገድ ሲያስተላልፍ ቆይቶ በሥርጭቱ የሞገድ ጥራት ማነስ ምክንያት ዝግጅቱን በማቋረጥ ጉዳዩን ሲያጠና ቆይቷል። ከረዥም ጊዜ ጥናት በኋላ በተሻለ የሬዲዮ ሞገስ ለማስተላለፍ የሚያስችለውን ቴክኒካዊ እና ሌሎች መሰል ዝግጅቶችን ሲያከናውን ቆይቶ አሁን ዝግጅቱን ለመጀመር ከመጨረሻው ደረጃ ላይ መድረሱን ማኅበሩ አረጋግጧል። ለዚህ አገልግሎት ሁነኛ ሚና በመጫወት ላይ የሚገኘው የአሜሪካ ማዕከል አባላትም፥ ስለ ሬዲዮው የተደረገውን ገለጻ በመከታተል ከእነርሱ የሚፈለገውን ነገር በመቀበልና ለተግባራዊነቱ ውሳኔ በማሳለፍ አጀንዳው ተጠናቋል።
የ2004 ዓ.ምሕረትን የአገልግሎት ዕቅድ ያደመጠው የማዕከሉ ጠቅላላ ጉባኤ በመጪው ዓመት “የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን አስተዋጽዖ ለኢትዮጵያ” የሚል ዐውደ ርእይ ይካሔድ ዘንድ የቀረበውን ዕቅድ እንዲሁም ስለ ሕጻናት ትምህርት፣ ስለ ስብከተ ወንጌል፣ ስለ ድረ ገጾች መጠናከር፣ በአሜሪካ የሚገኙትን አህጉረ ስብከት ስለመርዳት፣ ቃለ እግዚአብሔርን በመጻሕፍት፣ በጋዜጦችና በተለያዩ የሕትመት ውጤቶች ስለማሰራጨት፣ ሰንበት ት/ቤቶችን ስለመርዳት ወዘተ በጠቅላላው በየአገልግሎት ክፍሎቹ የቀረቡለት ዕቅዶች ላይ ተወያይቶ አጽድቋቸዋል።
ከማዕከሉ አገልግሎት ክፍሎች በተጨማሪ ማዕከሉ ባሉት 11 “ቀጣና ማዕከላት” የተዘጋጁትን ዕቅዶች ተመልክቶ ማሻሻዎችን በማድረግ አጽድቋቸዋል። የ2003 ዓ/ምሕረት አገልግሎትን በተመለከተ የኦዲት እና ኢንስፔክሽንን ሪፖርት አድምጧል። በዚህም ድክመት በታየባቸው የአገልግሎት ዘርፎች ላይ ችግሮችን ለማቃለል የሚያስችሉ መፍትሔዎችን ጉባኤው ለግሷል።
በእንግድነት ከአዲስ አበባ በመጡት በመልአከ ሰላም ጌታቸው ደጀኔ ትምህርት ከመሰጠቱም በላይ፥ የሰሜን አሜሪካ የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት መልእክትም በተወካዩዋ አማካይነት በንባብ ተሰምቷል።
ጉባኤውን በታላቅ ንቃት የተከታተሉት የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ አብርሃምም በሰጡት ቃለ ምዕዳን በስጋት እና በፍርሃት መሠራት ያለባቸውን ሥራዎች ከመሥራት ወደ ኋላ ማለት እንደማይገባ መክረው ማዕከሉ የጀመረውን አገልግሎት አጠናክሮ ይቀጥል ዘንድ መመሪያ ሰጥተዋል። ጉባኤው በሚከናወንባቸው ጊዜያት በሙሉ እንደማይለዩ፣ ጉዳዩ የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት እስከሆነ ድረስ በተልዕኮው ከማኅበሩ ጎን እንደሚቆሙ በማስረዳት ጉባኤተኛውን አበረታተዋል።
የዚህ ዓመት ጠቅላላ ጉባኤ ሲጠናቀቅም 14ኛውን ጉባኤ በዴንቨር ለማካሄድ ባለተራው ጽዋውን ሲወስድ የሜኔሶታ ቀ/ማዕከል በበኩሉ 15ኛውን ለማዘጋጀት “ማነህ ባለ ሣምንት” የሚለውን ጥሪ ተቀብሏል። “ያብጽዐነ አመ ከመ ዮም …” በሚለው ተስፋ አዘል መዝሙር በቀነ ቀጠሮ ጉባኤተኛው ስብሰባውን አጠናቆ ወደየመጣበት በሰላም ተመልሷል። 

የሐዋሳ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ችግር ፊጥረዋል ባላቸው ላይ ውሳኔ አሳለፈ

በተ/ሥላሴ ጸጋ ኪሮስ
በከሳሽ የሐዋሳ ከተማ አቃቤ ሕግ እና በሐዋሳ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን በተፈጠረው ግጭት ከፍተኛ የአካል ጉዳት አድርሰዋል ተብለው በተከሰሱት በሐዋሳ ከፍተኛ ፍርድ ቤት የተካሄደው ክርክር ውሳኔ አገኘ፡፡

ትናንት ግንቦት 25 ቀን 2003 ዓ.ም በዋለው ችሎት በከሳሽ የሐዋሳ ከተማ አቃቤ ሕግ በኩል የሰውና የተለያዩ ማስረጃዎች የቀረበ ሲሆን ተከሳሾቹ መከላከል እንዳልቻሉ ምንጮቻችን ገልጸዋል፡፡
ከግራና ከቀኝ ክርክሮችን ያደመጠው ችሎት የተስፋ ኪዳነ ምሕረት ሰብሳቢ በሆነው ገዛኸኝ አበራ ላይ የ8 ዓመት፣ አየነው ወ/ሚካኤል ላይ 8 ዓመት፣ አቶ ተስፋዬ ገ/መድህን ላይ የ3 ዓመት እንዲሁም ጌታሁን ተፈራ ላይ የ5 ዓመት የእስራት ብይን ሰጥቷል፡፡
ተከሳሾቹ ምንም ዓይነት የመፀፀትና የመመለስ አዝማሚያ ባለማሳየታቸው ቅጣቱ ሊከብድባቸው እንደቻለ ተገልጿል፡፡
በተያያዘም አዲስ የተሾሙት የሲዳማ አማሮ ቡርጂ ዞኖችና ልዩ ወረዳዎች ሥራ አስኪያጅ ትናንት ወደ ተመደቡበት ሀገረ ስብከት ደርሰዋል፡፡
ብፁዕ አቡነ በርናባስ፣ የካቲት 12 2003 ዓ.ም

የምዕራብ ጎጃም ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ በርናባስ አጭር የሕይወት ታሪክ

ከባሕር ዳር ማዕከል

ግንቦት23፣ 2003ዓ.ም

ብፁዕ አቡነ በርናባስ ግንቦት 20 ከምሽቱ 3.00 ማረፋቸው ይታወሳል፡፡

ብፁዕ አቡነ በርናባስ፣ የካቲት 12 2003 ዓ.ምየብፁዕነታቸው የቀብር ሥነ ሥርዓት ግንቦት 22 ቀን 2003 ዓ.ም የተፈጸመ ሲሆን በሥርዓቱ ላይ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ብፁዕ አቡነ ገሪማ፣ ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል፣  ብፁዕ አቡነ አረጋዊ፣ ብፁዕ አቡነ ኤልሣዕ  ብፁዕ አቡነ ሄኖክ፣ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ፣ ብፁዕ አቡነ ማርቆስ እንዲሁም የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አያሌው ጎበዜና የክልሉ ባለ ሥልጣናት፣ ከአዲስ አበባ የመጡ የደብር አስተዳዳሪዎች፣ የቅድስት ሥላሴ ኮሌጅ የመጻሕፍት ትርጓሜ መምህር የሆኑት መምህር ደጉ ዓለም ካሣ፣  የማኅበረ ቅዱሳን ሥራ አመራር ጉባኤ ጸሐፊ አቶ ዘላለም አጥናፉ እንዲሁም ሌሎች በርካታ እንግዶችና ምዕመናን ተገኝተዋል፡፡

በቀብር ሥነ ሥርዓቱ ላይ በብፁዕነታቸው ጥረት የተመሠረተውና ሀገረ ስብከቱ የሚገኘው የቤዛ ብዙኃን አጸደ ሕፃናት ተማሪዎች፣ በማኅበረ ቅዱሳን የአቡነ ጎርጎርዮስ አጸደ ሕፃናትና አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪዎች እንዲሁም የማኅበረ ቅዱሳን ባሕር ዳር ማዕከል የባሕርዳር ዩኒቨርሲቲ ዋናው ግቢና ኢንጂነሪንግ ፋኩልቲ ግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች የአበባ ጉንጉን በመያዝ አስከሬናቸውን አጀበዋል፡፡

የብፁዕነታቸው የቀብር ሥነ ሥርዓት ከቀኑ 6.00 ላይ የሀገረ ስብኩቱ መንበር በሆነው በፈለገ ገነት ቅዱስ ጊዮርጊስ ገዳም ተፈጽሟል፡፡

 

Abune Bernabas.jpg

የምዕራብ ጎጃም ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ በርባናስ አረፉ

በተ/ሥላሴ ጸጋ ኪሮስ
ግንቦት 21/2003 ዓ.ም.
Abune Bernabas.jpgከሃያ ዓመታት በላይ ቤተ ክርስቲያንን በጵጵስና በቅንነት ያገለገሉት የምዕራብ ጎጃም ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የነበሩት ብፁዕ አቡነ በርናባስ አረፉ፡፡

ርክበ ካህናትን ተከትሎ የሚደረገውን የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ ለመካፈል ወደ አዲስ አበባ መጥተው በነበሩበት ወቅት ታመው እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡ በዚህም ሳቢያ የምልዐተ ጉባኤውን የመጨረሻውን ቀን ማለትም የማክሰኞ ዕለት ስብስባ አልተካፈሉም፡፡ በዚህም ሁኔታ አርብ ግንቦት 19 ቀን 2003 ዓ.ም. ከአዲስ አበባ ተነስተው የምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ከሆኑት ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ጋር ደብረ ማርቆስ ገብተው ያደሩ ሲሆን ወደ ሀገረ ስብከታቸው መቀመጫ ባሕር ዳር  ቅዳሜ 8፡00 ሰዓት ገብተው በመዋል ማታ 1፡30 ላይ እንዳረፉ ታውቋል፡፡

እረፍታቸው ከተሠማ በኋላ በዛሬው ዕለት የክልሉ ርዕሰ መስተዳደር አቶ አያሌው ጎበዜ ከሌሎች ባለስልጣናት ጋር በሀገረ ስብከቱ ግቢ ውስጥ በሚገኘው የብፁዕነታቸው መኖሪያ ቤት ሀዘንተኛውን አጽናንተዋል፡፡
 
የቀብር ሥነ ሥርዓቱም ሰኞ ግንቦት 22 ቀን 2003 ዓ.ም በባሕር ዳር ፈለገ ገነት ቅዱስ ጊዮርጊስ ገዳም  የሚፈፀም  ሲሆን  ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት የዓለም ሃይማኖቶች ምክር ቤት ፕሬዝዳንት የዓለም ሃይማኖቶች ለሰላም የክብር ፕሬዝዳንት፣ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ የመንግስት ባለስልጣናትና ምዕመናን በሚገኙበት ይፈጸማል፡፡

ብፁዕ አቡነ በርባናስ የተወለዱት በምዕራብ ጎጃም ዞን ቡሬ ወረዳ ልዩ ስሙ ፉቢ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ በ1911 ዓ.ም. ሲሆን፥ በ1983 ዓ.ም. በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ፓትርያርክ አንብሮተ እድ ጵጵስና ተሹመው በተለያዩ ኃላፊነቶች እስከ ዛሬዋ ቀን ድረስ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን አገልግለዋል፡፡