“አብዝቶ የመመገብ ጣጣው”

  (በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ)
ግንቦት 30/2003 ዓ.ም.

ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ

መግቢያ

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የዮሐንስን ወንጌል በተረጎመበት በ21ኛው ድርሳኑ “ ጌታችን በእናታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ጥያቄ በቃና ሰርግ ላይ ስለምን ውሃውን ወደ ወይን ጠጅነት እንደቀየረው  ከአብራራ በኋላ ከዛሬ 1500 ዓመት በፊት በአሁኑ ጊዜ እንደ አዲስ ግኝት ተደርገው የሚታዩትን አብዝቶ በመመገብ የሚመጡትን የጤና ጉድለቶች ጽፎልን እናገኛለን ፡፡ ጽሑፉ ተተርጉሞ እንዲህ ቀርቦአል።

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ውሃውን ወደ ወይን ጠጅነት ያኔ እንደቀየረ ዛሬም እኛን ድካማችንንና እንደ ወራጅ ውሃ በአንድ ቦታ ጸንቶ መቆየት የተሣነውን የሥጋ ፈቃዳችንን ከመቀየር አልተቆጠበም ፡፡ ዛሬም አዎን ዛሬም ልክ እንደ ወራጅ ውሃ ቀዝቃዛ ፣የፈጠነና ፣ ያልተረጋጋ ጠባይ ያላቸው ሰዎች አሉ ፡፡ እነዚህን ፈቃዶቻችንን ወደ ጌታችን እናምጣቸው ፤ እርሱ ወደ ወይንነት ይቀይራቸዋል፡፡ ከዚያም በኋላ ውኃ ሆነው ከእንግዲህ አይቀጥሉም ፡፡ ነገር ግን ለራሳቸውና ለሌሎች ደስታን የሚሰጡ አካላት ይሆናሉ ፡፡

ባልተረጋጋ ውሃ የተመሰሉት እነማን ናቸው ? ለዚህ ከንቱ ዓለም ሕሊናቸውን ያስገዙ ወገኖች ፣ የዚህን ዓለምን ቅምጥልነት ፣ አለቅነትንና ክብርን የሚሹ ናቸው፡፡ እነዚህ ፍቃዶቻችን እንደውኃ የሚፈሱ ፣ ፈጽሞ ያልተረጋጉ ፣ ለአመፃ የሚፋጠኑ ቁልቁል የሚምዘገዘጉ ውኆች ናቸው ፡፡
 
ዛሬ ሀብታም የነበረው ነገ ደሃ ይሆናል ፡፡ በአንድ ወቅት ዝናው ሲነገርለት፣ የተጌጠና የተንቆጠቆጠ ልብስ ለብሶ በሰረገላ ላይ የሚሄድና ብዙ አጃቢዎች የነበሩት ሰው ፣ ያለፈቃዱ ያን የተዋበ መኖሪያውን ተቀምቶ ወደ ወይኒ ተጥሎ ይገኛል ፡፡ ለሥጋው ደስታ የሚተጋው ሆዳሙ ደግሞ የሥጋ ፈቃዱን ከሞላ በኋላ ሆዱ ሳይጎድልበት ለአንድ ቀን መቆየት አይቻለውም ፡፡ ነገር ግን እነዚህ ምግቦች ከሆዱ ሲጠፉ ወደ ቀድሞው ምቾቱ ለመመለስ ሲል ከፊት ይልቅ አብዝቶ ይመገባል ፡፡ አመጋገቡም ሁሉን ጠራርጎ እንደሚበላ እንደጎርፍ ውሃ ነው ፡፡ በዝናብ ወቅት የሚነሣው ጎርፍ አስቀድሞ የነበረ ውሃ በከፈተለት ጎዳና ገብቶ ቦታውን ሁሉ ያጥለቀልቀዋል ፡፡ እንዲሁ በሆዳሙም ዘንድ እንዲህ ይሆናል ፡፡ አስቀድሞ የነበረው ሲጠፋ እርሱ በቀደደው ሌሎች  የሥጋ ፍቃዶች በዝተው ይገባሉ ፡፡
 
 ምድራዊው ነገር ይህን ይመስላል ፤ መቼም ቢሆን የተረጋጋ አይደለም ፡፡ መቼም ቢሆን አንዱ ሌላውን እየተካ የሚፈስ እና የሚቸኩል ነው ፡፡ ነገር ግን የቅምጥልነትን ኑሮ በተመለከተ ጣጣው በከንቱ መባከን ወይም መቻኮል ብቻ አይደለም ፡፡ ሌሎችም እኛን ከመከራ የሚጥሉን ችግሮችም አሉበት ፡፡ ቅምጥልነት ባመጣብን ጣጣ የሰውነት አቅማችን ይዳከማል ፣ እንዲሁም የነፍስ ጠባይዋም ይለወጣል ፡፡ ከባድ ጎርፍ ወንዙን በደለል ወዲያው እንደማይሞላው  ፣ ቀስ በቀስ ግን እንዲሞላው ፣ እንዲሁ ቅምጥልነትና ዋልጌነት እንደ አልማዝ ብርቱ የሆነውን ጤንነታችንን ቀስ በቀስ ውጦ ያጠፋዋል ፡፡
 
 ወደ ሐኪም ዘንድ ሄደህ ብትጠይቅ የበሽታዎች ሁሉ ምንጫቸው አብዝቶ ከመመገብ እንደሚመነጩ ይነግሩሃል ፡፡ ጠግቦ አለመብላትና ለሆድ የማይከብዱ ምግቦችን መመገብ ለጤንነት እናት ነው ፡፡ ስለዚህም የሕክምና ባለሙያዎች የጤንነት እናት ብለው ይጠሩታል ፡፡ እናም ጠግቦ አለመብላት የጤንነት እናት ከሆነ  ፣ አብዝቶ መመገብ ደግሞ የበሽታዎች ሁሉ እናት እንደሆነ በዚህ ይታወቃል፡፡ አብዝቶ መመገብ ሰውነታችንን አዳክሞ በሕክምና ባለሙያ እንኳ ለማይድን በሽታ አጋልጦ ይሰጠናል ፡፡
 
አብዝቶ መመገብ ለሪህ ፣ ለአእምሮ ውስጥ የደም መፍሰስ ፣ ለዐይን የማየት ኃይል መቀነስ ፣ ለእጅ መዛል ፣ ለአካል ልምሾነት  ፣ ለቆዳ መንጣት (ወደ ቢጫነት መቀየር  ፤ በተለምዶ የጉበት በሽታ ለምንለው ምልክት ነው ተብሎ ይታመናል ) ስጉና ድንጉጥ መሆን ፣ ለኃይለኛ ትኩሳት እና ከጠቀስናቸው በላይ ለሆኑ ሌሎች ሕመሞች ያጋልጣል ፡፡ በዚህ የሚመጡትን የጤንነት ጠንቆች በዚች ሰዓት ውስጥ ዘርዝሮ ለመጨረስ ጊዜው አይበቃም ፡፡ እነዚህ ሁሉ ሕመሞች በተፈጥሮአችን ላይ የሚከሰቱት መጥኖ በመብላት ወይም በጾም አይደለም ፡፡ ነገር ግን ከሆዳምነታችንና ከአልጠግብ ባይነታችን የተነሣ የሚመጡብን ናቸው ፡፡ በእነዚህ ምክንያቶች የተነሣ በነፍሳችን ላይ የሚከሰቱብንን  በሽታዎች ብንመለከት ዋዘኝነት ፣ ስንፍና ፣ ድንዛዜ ፣ የሥጋ ፍትወቶቻችን ማየል፣ እነዚህንና የመሳሰሉ ሕመሞች ነፍሳችንን ያጠቁዋታል ፡፡ ለእነዚህ ሁሉ ምንጫቸው ሳይመጥኑ አብዝቶ መመገብ ነው ፡፡ ከእንዲህ ዐይነት ቅጥ ያጣ አመጋገብ  በኋላ የቅምጥሎች ነፍስ ክፉ አውሬዎች ሥጋዋን ተቀራምተው ከተመገቡዋት አህያ ያልተሻለች ትሆናለች ፡፡ ቅምጥሎችን ስለሚጠብቃቸው  ሕመሞችና ስቃዮች ጨምሬ ልናገርን ? ከብዛታቸው የተነሣ ዘርዝሬ መጨረስ አይቻለኝም ፡፡
 ነገር ግን በአንድ ማጠቃለያ አሳብ ሁሉንም ግልጽ አድርጌ ማስረዳት እፈልጋለሁ ፡፡ እንዲህ ከሚያደርጉ ከቅምጥሎች ማዕድ ማንም ደስ ብሎት አይመገብ ፡፡ አስቀድመን እንደተነጋገርነው ጾምና መጥኖ መመገብ የደስታና የጤንነት ምንጮች ሲሆኑ ያለቅጥ መመገብ ግን የበሽታና የደስታ ማጣት ሥር እና ምንጭ ናቸውና ፡፡
ሁሉ ነገር ከተሟላልን ፍላጎት የለንም ፡፡ ፍላጎት ከሌለ ደግሞ እንዴት ደስታን ልናገኛት እንችላለን ? ስለዚህም ድሆች ከባለጠጎች ይልቅ የተሻለ ማስተዋልና ጤና ያላቸው ብቻ አይደሉም ፣ ነገር ግን ታላቅ በሆነ ደስታ ውስጥ የሚኖሩ ጭምር ናቸው ፡፡ ይህንን ከተረዳን ከመጠጥና ከቅምጥልነት ሕይወት ፈጥነን እንሽሽ ፣ ከማዕዱ ብቻ አይደለም ፣ ከዚህ ሕይወት ከሚገኙት ፍሬዎች ሁሉ እንሽሽ ፡፡  እነርሱን በመንፈሳዊ ሕይወት በሚገኘው ደስታ ለውጠን በቅድስና እንመላለስ  ፡፡ ነቢዩ “ በእግዚአብሔር ደስ ይበላችሁ እርሱ የልብህን  መሻት ይሰጥሃል”(መዝ.36፥4)  እንዳለው በጌታ ደስ ይበለን ፡፡ በዚህም ዓለም በሚመጣውም ዓለም በእርሱ በእግዚአብሔር መልካም ስጦታ ደስ ይለን ዘንድ የሰው ልጆችን በሚያፈቅረው በኩል ለእርሱ ለእግዚአብሔር አብ ለመንፈስ ቅዱስም ክብር ይሁን  እስከዘለዓለሙ ፡፡ አሜን !!          
   በነገራችን ላይ የሕክምና ባለሙያዎች እንዲሁም የፍልስፍና ምሁራን(ተማሪዎች) በዚህ በቅዱስ ዮሐንስ ገለጻ ላይ ምን ይላሉ ? በmkwebsitetechnique@gmail.com ጻፉልን።

በማ/ቅዱሳን የአሜሪካ ማዕከል ዓመታዊ ጠቅላላ ጉባኤ ውሳኔዎችን በማሳለፍ ተጠናቀቀ።

 
(የአሜሪካ ማዕከል፤ አትላንታ፤ ጆርጂያ)፦ “የቤተ ክርስቲያናችንን ህልውና መጠበቅ የሁላችንም ኃላፊነት ነው” በሚል መሪ ቃል ግንቦት 20, 21 እና 23/ 2003 ዓ.ም ሲካሔድ የቆየው በማ/ቅዱሳን የአሜሪካ ማዕከል ዓመታዊ ጠቅላላ ጉባኤ ውሳኔዎችን በማሳለፍ እና የ2004 ዓ.ምሕረትን ዕቅድ በማጽደቅ ተጠናቀቀ።

ለ13ኛ ጊዜ በተካሔደው እና የዲሲ እና አካባቢው ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ አብርሃም፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን አበው፣ ዲያቆናት ወንድሞች፣ የማኅበሩ አባላት ወንድሞች እና እህቶች እንዲሁም ተጋባዥ እንግዶች በተገኙበት የተካሔደው ጉባኤ የማዕከሉን የ2003 ዓ.ም ዓመታዊ የተግባር ድርጊቶች ሪፖርት ከማዳመጡም በላይ በቀረቡት ሪፖርቶች ላይ ውይይት አድርጓል። “የማዕከላችን የአገልግሎት ተግዳሮቶች እና የመፍትሔ አቅጣጫዎች”፣ “የማኅበሩ አባላት ማሕበራዊ ተሳትፎ” እንዲሁም “የቤተ ክርስቲያን አንድነት” በሚሉ ርእሶች ዙሪያ ትምህርቶች ተሰጥተው ውይይቶች ተደርጎባቸዋል።
 
ወደ ኢትዮጵያ ስለሚተላለፍ ሳምንታዊ የሬዲዮ ፕሮግራም ጉዳይ በሰፊው ተወያይቷል። የተዋሕዶ ድምጽ/ድምፀ ተዋሕዶ/ በመባል ስለተሰየመው እና በሳምንት ሁለት ቀን ወደ ኢትዮጵያ መተላለፍ ስለሚጀምረው የሬዲዮ ጣቢያ ጉዳዩ የሚመለከታቸው አባላት ያጠኑት ጥልቅ ጥናት ከቀረበ በኋላ ሰፊ ውይይት ተደርጎበታል።
ማኅበሩ ከዚህ በፊት ለአንድ ዓመት ያህል የሬዲዮ ዝግጅት በአጭር ሞገድ ሲያስተላልፍ ቆይቶ በሥርጭቱ የሞገድ ጥራት ማነስ ምክንያት ዝግጅቱን በማቋረጥ ጉዳዩን ሲያጠና ቆይቷል። ከረዥም ጊዜ ጥናት በኋላ በተሻለ የሬዲዮ ሞገስ ለማስተላለፍ የሚያስችለውን ቴክኒካዊ እና ሌሎች መሰል ዝግጅቶችን ሲያከናውን ቆይቶ አሁን ዝግጅቱን ለመጀመር ከመጨረሻው ደረጃ ላይ መድረሱን ማኅበሩ አረጋግጧል። ለዚህ አገልግሎት ሁነኛ ሚና በመጫወት ላይ የሚገኘው የአሜሪካ ማዕከል አባላትም፥ ስለ ሬዲዮው የተደረገውን ገለጻ በመከታተል ከእነርሱ የሚፈለገውን ነገር በመቀበልና ለተግባራዊነቱ ውሳኔ በማሳለፍ አጀንዳው ተጠናቋል።
የ2004 ዓ.ምሕረትን የአገልግሎት ዕቅድ ያደመጠው የማዕከሉ ጠቅላላ ጉባኤ በመጪው ዓመት “የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን አስተዋጽዖ ለኢትዮጵያ” የሚል ዐውደ ርእይ ይካሔድ ዘንድ የቀረበውን ዕቅድ እንዲሁም ስለ ሕጻናት ትምህርት፣ ስለ ስብከተ ወንጌል፣ ስለ ድረ ገጾች መጠናከር፣ በአሜሪካ የሚገኙትን አህጉረ ስብከት ስለመርዳት፣ ቃለ እግዚአብሔርን በመጻሕፍት፣ በጋዜጦችና በተለያዩ የሕትመት ውጤቶች ስለማሰራጨት፣ ሰንበት ት/ቤቶችን ስለመርዳት ወዘተ በጠቅላላው በየአገልግሎት ክፍሎቹ የቀረቡለት ዕቅዶች ላይ ተወያይቶ አጽድቋቸዋል።
ከማዕከሉ አገልግሎት ክፍሎች በተጨማሪ ማዕከሉ ባሉት 11 “ቀጣና ማዕከላት” የተዘጋጁትን ዕቅዶች ተመልክቶ ማሻሻዎችን በማድረግ አጽድቋቸዋል። የ2003 ዓ/ምሕረት አገልግሎትን በተመለከተ የኦዲት እና ኢንስፔክሽንን ሪፖርት አድምጧል። በዚህም ድክመት በታየባቸው የአገልግሎት ዘርፎች ላይ ችግሮችን ለማቃለል የሚያስችሉ መፍትሔዎችን ጉባኤው ለግሷል።
በእንግድነት ከአዲስ አበባ በመጡት በመልአከ ሰላም ጌታቸው ደጀኔ ትምህርት ከመሰጠቱም በላይ፥ የሰሜን አሜሪካ የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት መልእክትም በተወካዩዋ አማካይነት በንባብ ተሰምቷል።
ጉባኤውን በታላቅ ንቃት የተከታተሉት የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ አብርሃምም በሰጡት ቃለ ምዕዳን በስጋት እና በፍርሃት መሠራት ያለባቸውን ሥራዎች ከመሥራት ወደ ኋላ ማለት እንደማይገባ መክረው ማዕከሉ የጀመረውን አገልግሎት አጠናክሮ ይቀጥል ዘንድ መመሪያ ሰጥተዋል። ጉባኤው በሚከናወንባቸው ጊዜያት በሙሉ እንደማይለዩ፣ ጉዳዩ የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት እስከሆነ ድረስ በተልዕኮው ከማኅበሩ ጎን እንደሚቆሙ በማስረዳት ጉባኤተኛውን አበረታተዋል።
የዚህ ዓመት ጠቅላላ ጉባኤ ሲጠናቀቅም 14ኛውን ጉባኤ በዴንቨር ለማካሄድ ባለተራው ጽዋውን ሲወስድ የሜኔሶታ ቀ/ማዕከል በበኩሉ 15ኛውን ለማዘጋጀት “ማነህ ባለ ሣምንት” የሚለውን ጥሪ ተቀብሏል። “ያብጽዐነ አመ ከመ ዮም …” በሚለው ተስፋ አዘል መዝሙር በቀነ ቀጠሮ ጉባኤተኛው ስብሰባውን አጠናቆ ወደየመጣበት በሰላም ተመልሷል። 

የሐዋሳ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ችግር ፊጥረዋል ባላቸው ላይ ውሳኔ አሳለፈ

በተ/ሥላሴ ጸጋ ኪሮስ
በከሳሽ የሐዋሳ ከተማ አቃቤ ሕግ እና በሐዋሳ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን በተፈጠረው ግጭት ከፍተኛ የአካል ጉዳት አድርሰዋል ተብለው በተከሰሱት በሐዋሳ ከፍተኛ ፍርድ ቤት የተካሄደው ክርክር ውሳኔ አገኘ፡፡

ትናንት ግንቦት 25 ቀን 2003 ዓ.ም በዋለው ችሎት በከሳሽ የሐዋሳ ከተማ አቃቤ ሕግ በኩል የሰውና የተለያዩ ማስረጃዎች የቀረበ ሲሆን ተከሳሾቹ መከላከል እንዳልቻሉ ምንጮቻችን ገልጸዋል፡፡
ከግራና ከቀኝ ክርክሮችን ያደመጠው ችሎት የተስፋ ኪዳነ ምሕረት ሰብሳቢ በሆነው ገዛኸኝ አበራ ላይ የ8 ዓመት፣ አየነው ወ/ሚካኤል ላይ 8 ዓመት፣ አቶ ተስፋዬ ገ/መድህን ላይ የ3 ዓመት እንዲሁም ጌታሁን ተፈራ ላይ የ5 ዓመት የእስራት ብይን ሰጥቷል፡፡
ተከሳሾቹ ምንም ዓይነት የመፀፀትና የመመለስ አዝማሚያ ባለማሳየታቸው ቅጣቱ ሊከብድባቸው እንደቻለ ተገልጿል፡፡
በተያያዘም አዲስ የተሾሙት የሲዳማ አማሮ ቡርጂ ዞኖችና ልዩ ወረዳዎች ሥራ አስኪያጅ ትናንት ወደ ተመደቡበት ሀገረ ስብከት ደርሰዋል፡፡
ብፁዕ አቡነ በርናባስ፣ የካቲት 12 2003 ዓ.ም

የምዕራብ ጎጃም ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ በርናባስ አጭር የሕይወት ታሪክ

ከባሕር ዳር ማዕከል

ግንቦት23፣ 2003ዓ.ም

ብፁዕ አቡነ በርናባስ ግንቦት 20 ከምሽቱ 3.00 ማረፋቸው ይታወሳል፡፡

ብፁዕ አቡነ በርናባስ፣ የካቲት 12 2003 ዓ.ምየብፁዕነታቸው የቀብር ሥነ ሥርዓት ግንቦት 22 ቀን 2003 ዓ.ም የተፈጸመ ሲሆን በሥርዓቱ ላይ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ብፁዕ አቡነ ገሪማ፣ ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል፣  ብፁዕ አቡነ አረጋዊ፣ ብፁዕ አቡነ ኤልሣዕ  ብፁዕ አቡነ ሄኖክ፣ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ፣ ብፁዕ አቡነ ማርቆስ እንዲሁም የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አያሌው ጎበዜና የክልሉ ባለ ሥልጣናት፣ ከአዲስ አበባ የመጡ የደብር አስተዳዳሪዎች፣ የቅድስት ሥላሴ ኮሌጅ የመጻሕፍት ትርጓሜ መምህር የሆኑት መምህር ደጉ ዓለም ካሣ፣  የማኅበረ ቅዱሳን ሥራ አመራር ጉባኤ ጸሐፊ አቶ ዘላለም አጥናፉ እንዲሁም ሌሎች በርካታ እንግዶችና ምዕመናን ተገኝተዋል፡፡

በቀብር ሥነ ሥርዓቱ ላይ በብፁዕነታቸው ጥረት የተመሠረተውና ሀገረ ስብከቱ የሚገኘው የቤዛ ብዙኃን አጸደ ሕፃናት ተማሪዎች፣ በማኅበረ ቅዱሳን የአቡነ ጎርጎርዮስ አጸደ ሕፃናትና አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪዎች እንዲሁም የማኅበረ ቅዱሳን ባሕር ዳር ማዕከል የባሕርዳር ዩኒቨርሲቲ ዋናው ግቢና ኢንጂነሪንግ ፋኩልቲ ግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች የአበባ ጉንጉን በመያዝ አስከሬናቸውን አጀበዋል፡፡

የብፁዕነታቸው የቀብር ሥነ ሥርዓት ከቀኑ 6.00 ላይ የሀገረ ስብኩቱ መንበር በሆነው በፈለገ ገነት ቅዱስ ጊዮርጊስ ገዳም ተፈጽሟል፡፡

 

Abune Bernabas.jpg

የምዕራብ ጎጃም ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ በርባናስ አረፉ

በተ/ሥላሴ ጸጋ ኪሮስ
ግንቦት 21/2003 ዓ.ም.
Abune Bernabas.jpgከሃያ ዓመታት በላይ ቤተ ክርስቲያንን በጵጵስና በቅንነት ያገለገሉት የምዕራብ ጎጃም ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የነበሩት ብፁዕ አቡነ በርናባስ አረፉ፡፡

ርክበ ካህናትን ተከትሎ የሚደረገውን የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ ለመካፈል ወደ አዲስ አበባ መጥተው በነበሩበት ወቅት ታመው እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡ በዚህም ሳቢያ የምልዐተ ጉባኤውን የመጨረሻውን ቀን ማለትም የማክሰኞ ዕለት ስብስባ አልተካፈሉም፡፡ በዚህም ሁኔታ አርብ ግንቦት 19 ቀን 2003 ዓ.ም. ከአዲስ አበባ ተነስተው የምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ከሆኑት ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ጋር ደብረ ማርቆስ ገብተው ያደሩ ሲሆን ወደ ሀገረ ስብከታቸው መቀመጫ ባሕር ዳር  ቅዳሜ 8፡00 ሰዓት ገብተው በመዋል ማታ 1፡30 ላይ እንዳረፉ ታውቋል፡፡

እረፍታቸው ከተሠማ በኋላ በዛሬው ዕለት የክልሉ ርዕሰ መስተዳደር አቶ አያሌው ጎበዜ ከሌሎች ባለስልጣናት ጋር በሀገረ ስብከቱ ግቢ ውስጥ በሚገኘው የብፁዕነታቸው መኖሪያ ቤት ሀዘንተኛውን አጽናንተዋል፡፡
 
የቀብር ሥነ ሥርዓቱም ሰኞ ግንቦት 22 ቀን 2003 ዓ.ም በባሕር ዳር ፈለገ ገነት ቅዱስ ጊዮርጊስ ገዳም  የሚፈፀም  ሲሆን  ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት የዓለም ሃይማኖቶች ምክር ቤት ፕሬዝዳንት የዓለም ሃይማኖቶች ለሰላም የክብር ፕሬዝዳንት፣ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ የመንግስት ባለስልጣናትና ምዕመናን በሚገኙበት ይፈጸማል፡፡

ብፁዕ አቡነ በርባናስ የተወለዱት በምዕራብ ጎጃም ዞን ቡሬ ወረዳ ልዩ ስሙ ፉቢ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ በ1911 ዓ.ም. ሲሆን፥ በ1983 ዓ.ም. በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ፓትርያርክ አንብሮተ እድ ጵጵስና ተሹመው በተለያዩ ኃላፊነቶች እስከ ዛሬዋ ቀን ድረስ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን አገልግለዋል፡፡

ሐዊረ ሕይወት መንፈሣዊ ጉዞ ቁጥር 2

ሐዊረ ሕይወት ቁጥር 2 መንፈሣዊ ጉዞ

ሐዊረ ሕይወት መንፈሣዊ ጉዞ ቁጥር 2

   

“በእንተ ጦማረ ሐሰት”

ግንቦት 13፣ 2003 ዓ.ም

በሐሰት የተሠራጨውን ሰነድ በተመለከተ ከማኅበረ ቅዱሳን የተሰጠ መግለጫ

እምነትና ሥርዓቷ ጸንቶ የቆየውን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሕልውናዋን ለማሳጣት እና ሐዋርያዊ ተልእኮዋን ለማደናቀፍ ቀን ከሌሊት የሚተጉ አካላት የጥፋት ሤራቸውን ከመጎንጎን እና የተቻላቸውን ሁሉ ከመፈጸም ወደ ኋላ ብለው አያውቁም፡፡ ቅድስት ቤተክርቲያን ሕግና ደንብ አውጥታ በመዋቅሯ አቅፋ እንዲያገለግል አደራና ሓላፊነት የሰጠችው ማኅበረ ቅዱሳንም የጥቃታቸው አንዱ አላማ ነው፡፡ የማኅበሩን ቀና አገልግሎት ለማስቆም ብዙ ጥረዋል፡፡
 
በእግዚአብሔር ፈቃድና ቸርነት የተመሠረተ እንደመሆኑ የቅድስት ቤተክርቲያንን መመሪያ ጠብቆ በአባቶች ምክርና ጸሎት እየታገዘ አገልገሎቱን ከመፈጸም ወደኋላ አይልም፡፡ እነዚህ የቅድስት ቤተክርስቲያንን ሐዋርያዊ አገልግሎት የሚፈታተኑ አካላት የማኅበረ ቅዱሳንን ስም በማጥፋት እንደደከሙት ሁሉ፤ ሰሞኑን የማኅበሩን ማኅተም በተጭበረበረ ሁኔታ / ፎርጅድ/ በመጠቀም፣ "የማኅበሩ የሃያ አምስት ዓመት እቅድ" ነው በማለት የሐሰት ሰነድ አዘጋጅተው በኢንተርኔት ለማሠራጨት እና ለተወሰኑ ብፁዓን አባቶች እንዲደርስ ለማድረግ ሞክረዋል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎቱ ሁሉ ግልጽ ነው፡፡ ባሳለፋቸው አሥራ ዘጠኝ የአገልግሎት ዓመታት እቅድና አፈጻጸሙ በየደረጃው ለሚገኙ የቤተክርስቲያን አካላት እና አባቶች እንዲሁም ለማኅበሩ ማእከላትና አባላት በየወቅቱ በሪፖርት የሚገለጽ ውይይት የሚደረግበት ሲሆን በዚሁ ሁኔታ ተግባራዊ የሚሆን ነው፡፡ ይህ የማኅበሩ አሠራር በተገቢው ሁኔታ ወደፊትም ይቀጥላል፡፡ ሰሞኑን የተሠራጨውን የሐሰት ጽሑፍ በተመለከተ የማኅበሩን መግለጫ እንደሚከተለው አቅርበነዋል፡፡ ሰሞኑን “ድንግል ማርያም” በተባለ የፌስ ቡክ አድራሻ(face book Account) “የማኅበረ ቅዱሳን የረዥም ጊዜ እቅድ” በሚል የተበተነ የሐሰት ጽሑፍ እንዲወጣ (Post) መደረጉ ታውቋል፡፡ ይህ ጽሑፍ በመጨረሻው ላይ የማኅበረ ቅዱሳን የሃያ አምስት ዓመት እቅድ እንደሆነ ይገልፃል፡፡ ለመሆኑ ይህ “ጦማረ ሐሰት” ምንጩ ከየት ነው? ጽሑፉ እንዳመለከተው በውኑ የማኅበረ ቅዱሳን እቅድ ነውን? ይዘቱና ዓላማውስ ምንድን ነው? ማኅበረ ቅዱሳንስ በዚህ ጽሑፍ ላይ ያለው አቋም ምንድን ነው?

ምንጩ ከየት ነው?
ጽሑፉ በራሱ ሥልጣን እየተጣጣረም ቢሆን ለመናገር የሚሞክረው "የማኅበረ ቅዱሳን ነኝ" እያለ ነው፡፡ ነገር ግን በመናገር እና በመሆን መካከል ያለውን ርቀት እንዳይፈራገጥ ባስገነዘው ጣእረ ሞት እንደያዘው የሚይዘውን የሚጨብጠውን ያጣ ወረቀት ነው፡፡ ለዚህም ጽሑፉ ሳያውቀው ምንጩን ሲናገር እናገኘዋለን፡፡ ይሁን እንጂ በመጀመሪያ ምንጩ ማኅበረ ቅዱሳን ሊሆን ይችላልን?

የሚለውን መመልከቱ አስፈላጊ ይሆናል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ከተመሠረተበት ጊዜ ጀምሮ እቅድ እያቀደ የእግዚአብሔርን አጋዥነት እየለመነ አገልግሎትን ሲያከናውን ቆይቷል፡፡ እቅድ ማቀድ በማኅበሩ ዘንድ እንግዳ ነገር አይደለም፡፡ በጥቂቱ የሃያ ዓመት ልምድም ያለው ማኅበር ነው፡፡ አባላቱም ከመንፈሳዊው አገልግሎት ባሻገር በየተሠማሩበት የሙያ ዘርፍ እቅድ እያቀዱ ራሳቸውን በዘመናዊው አሠራር ያበለጸጉ ከመሆናቸው አንጻር መሠረታዊ የእቅድ አዘገጃጀት እውቀት ያላቸው መሆኑን ልንጠራጠር አንችልም፡፡ የተበተነው ጽሑፍ ያውም ሁለት ከወገብ በታች /ግማሽ ገጽ/ የሆኑ ወረቀቶች ላይ ማኅበሩ የሃያ አምስት ዓመት እቅድ ተብሎ ተዘርዝሯል፡፡ እንዲህ አይነቱ የሃያ አምስት ዓመት እቅድ ማቀድ   በአዘጋጆቹ ዘንድ የተለመደ ይሆናል እንጂ በማኅበረ ቅዱሳን ዘንድ የለም፡፡ የማኅበሩ የአራት ዓመት ስልታዊ እቅድ እንኳን የተዘጋጀው በሃምሳ አምስት ገፆች ነው፡፡

ስልታዊ እቅድ እንደመሆኑ መጠን በዘመናዊው አሠራር የራሱ ቅርጽ (format) አለው፡፡ ቢያንስ ቢያንስ መግቢያ፣ የማኅበሩን ማንነት፣ የማኅበሩ ዓላማ፣ ርእይ፣ ተልእኮ፣ እሴት፣ የባለድርሻ አካላት ትንተና፣ ውጫዊ አካባቢ ትንታኔ፣ እንዲሁም አስፈላጊነቱ ሌሎች ትንታኔዎች ምቹ እና ፈታኝ ሁኔታዎች፣ የምቹ እና ፈታኝ ሁኔታዎች ምዘና፣ ወሳኝ ጉዳዮች፣ ስልታዊ እቅድ ዓላማ፣ ግብና ስልት፣ ዝርዝር የአፈጻጸም መርሐ ግብር እንዲሁም የክትትልና የግምገማ ሥርአት ያለው ሊሆን ይገባል፡፡

በዚህ ቅርጽ መሠረት የማኅበረ ቅዱሳን ስልታዊ /ስትራቴጂክ/ እቅዱን አዘጋጅቶ  ለሚመለከታቸው የቤተ ክርስቲያን አካላት በማቅረብ በእቅዱ መሠረት አገልግሎቱን በመፈጸም ላይ ይገኛል፡፡ ይሁን እንጂ ይህ አሠራሩ ያልተመቻቸው አካላት የጐንዮሽ እቅድ በማቀድ የራሳቸውን የፈጠራ ሥራ አቅርበዋል፡፡ማኅበረ ቅዱሳንን ለመወንጀል ታስቦ የሐሰት ሰነድ (forged document) ተዘጋጅቶ የተበተነበትም ምክንያት ያንን እቅድ አባቶች እንደማያውቁት በማስመሰል ነው፡፡

የፖለቲካ አጠቃቀም
ማኅበሩ በመዋቅሩ ሥር ያሉትን አካላት በራሱ መጥራት የተሳነው አስመስለው ቀርጸውታል፡፡ ለማሳያ የሚሆነውም በዝርዝር እቅዱ ውስጥ በአንድ ላይ "በየንዑሳን ቅርንጫፍ በኩል" የሚል ሐረግ ይገኛል፡፡ ሲጀምር ማኅበሩ ቅርንጫፍ የሚባል ምንም ዓይነት መዋቅር የለውም፡፡  
 
ከዋናው ማእከል ቀጥሎ ያሉት ማእከላት ይባላሉ እንጂ ንዑሳን አይባሉም፡፡ ይህም አጠቃቀሙ ሌላ አካል መሆኑን ያሳያል፡፡ በአስገራሚ ሁኔታ የተበተነው ወረቀት አንድ ተማሪ ክፍል ውስጥ ገብቶ ሲማር ከሚይዘው ማስታወሻ እንኳ ያነሰ፤ እቅድ መባል ካለበት እንኳ የጨነገፈ እቅድ ነው፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ሊያወጣው አይችልም፡፡ በዚህ መስፈርት እንኳን ቢታይ እቅዱ በምንም መለኪያ የማኅበረ ቅዱሳን አለመሆኑን ያረጋግጣል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ራሱን ሲጠራ ”ማህበረ ቅዱሳን” ብሎ አያውቅም። "እቅድ" የሚለውን ቃል አቅድ የሚለውን ተክቶ ለጥቅም እንዲውል አድርጐም አያውቅም፡፡ እነዚህን የተጠቀመው ጽሑፍ ራሱን እርቃኑን አቁሞ የማኅበረ ቅዱሳን አለመ ሆኑን የገለጠበት ዘርፍ ነው፡፡ ወረቀቱ ስለ እቅድ የሚናገር ከሆነ የተግባራዊነት ዘመኑ ከመቼ እስከ መቼ እንደሆነ እንኳ አለመገለጹ ድንገቴ እንደ ወራጅ ውኃ የፈሰሰ የጥቂቶች አሳብ እንጂ እቅድ አለመሆኑን ያሳብቅበታል፡፡ የስሕተት ሙሻዙር የጠመዘዛቸው አዘጋጆች እንደመሰላቸው እነርሱ ያስቀመጧቸውን በወንጀል ደረጃ የሚፈረጁ አደገኛ አሳቦች በማኅተም አትሞ በቲተር እና በፊርማ አስደግፎ ራሱን ለአደጋ አጋልጦ የሚያስቀምጥ ተቋም በሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን ይገኛል ብሎ ማሰብ ቂልነት ነው፡፡

በተሠራጨው እቅድ ላይ የተቀመጡት አሳቦች አሉታዊ እና አፍራሽ አስተሳሰቦች እንደመሆናቸው መጠን ማኅበሩ የቱንም ያክል ክፉ ነው ተብሎ ቢታሰብ እንኳ እንዲህ ያለ እቅድ በዚህ መልክ አዘጋጅቶ እና አንድ ቦታ አጠራቅሞ ይገኛል ተብሎ አይታሰብም፡፡ ያንን ያክል ክፋት ማርገዝ የቻለ እኩይ ሕሊና ቢኖር እንኳ አካሔዱን እና አቀማመጡን አይጠበብበትም ነበር የሚለው ለአንባቢ የሚተው ውሳኔ ይሆናል፡፡ እነዚህን አካሔዶች ጠቅልለን ስንመለከታቸው ምንጩ ለጊዜው የማኅበረ ቅዱሳንን በመጨረሻም የቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን ጥፋት ሌት ተቀን ከሚለማመኑ አካላት የተቀዳ ለመሆኑ ከቶውኑ ማን ይመራመራል? መጽሐፍ “በክፋታቸው እየባሱ ይሔዳሉ” እንዳለው የማኅበረ ቅዱሳን መኖር የእግር እሳት ስለሆነባቸው በምን መንገገድ ስሙን ቢያጠፉ ተቀባይነት ሊያገኙ እንደሚችሉ ሁልጊዜ ወጥመድ ያጠምዳሉ፡፡ እስካሁን ድረስ የእግዚአብሔር ቸርነት ከልክሏቸው አልተሳካላቸውም እንጂ የወገባቸው የሐሰት ዝናር ሲያልቅባቸው በማኅበሩ ወንበር ተቀምጠው የሚናገሩ በማስመሰል ማኅበሩ ቤተ ክርስቲያንን ለማጥፋት ተልእኮ እንዳለው አድርገው ሊያቅዱለት ፈለጉ፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ካባ ለብሰው ያቀዱለት እቅድ ግን ከተለመደው ክሳቸው የወጣ አለመሆኑ ነው፡፡

እስካሁን ድረስ ማኅበሩን ለምን ትቃወማላችሁ ሲባሉ ይሰጡት የነበረውን መልስ እቅድ ነው ብለው አቀረቡት እንጂ ምንም አዲስ ነገር አላመጡም፡፡ ስለሆነም በዚህ በጻፉት እቅዳቸው ምክንያት ማንም ሊደነግጥላቸው አይችልም፡፡ በተቻላቸው መጠን የመጨረሻዋን ጥይት ለመተኮስ ሲጥሩ መልሶ ራሳቸውን ወጋቸው፡፡ በተጉበትም መጠን በመጐዳታቸው አሟሟታቸውን ለማሳመር የሐሰት እና የጥፋት እቅድ ለማኅበሩ አወጡለት፡፡ የሚጠባበቁት ውጤት በእነዚያ ወንጀሎች ምክንያት ያቀዱለት አካል እለቱኑ ታንቆ እለቱኑ ሲሞት ለማየት በጉጉት ኮርቻ ላይ ተቀመጡ፤ የፈለጉት ማኅበሩ እነርሱ ጐን ቆሞ ቤተክርስቲያንን አንዲያጠፋላቸው ነበር፡፡

ግን ምን ያደርጋል? እነርሱም ታወቁ ሕልማቸውም መከነ፡፡ ራሱን በራሱ ሲቃረን አንድ  ተቋም ራሱን ሲገልጽ ‘እኛ” በሚል ባለቤት ሊናገር እንደ ሚችል የተረዳ ነገር ነው፡፡ በጽሑፉ ላይ ግን አባቶችን አባላት በማድረግና ”ስብሰባቸው ላይ” የሚል አባባል ተጠቅመዋል፡፡ ስለራሱ እቅድ የሚናገር ሰው ”በስብሰባችን ላይ” ይላል እንጂ ”ስብሰባቸው ላይ” እንዴት ሊል ይችላል? በተጨማሪም ”በራሱ ጠቅላላ ጉባኤ መምራት” በማለት ማኅበሩ ራሱን ”እርሱ” እያለ እንዲጠራ አድርገው ጽፈዋል፡፡ እንዲሁም ”ካህናቱን ለድርጅቱ ሠራተኞች አድርጐ መቅጠር” በሚለው እቅዳቸው ላይ ”እርሱ” ብሎ ራሱን እንዲጠራ አድርገውታል፡፡

ከእነዚህ አገላለጾች የምንረዳው የሆነ አካል ራሱን አስገድዶ የማኅበሩ አካል አድርጐ በመቁጠር ስለማኅበሩ ሆኖ እንዲጽፍ እንደተጨነቀ ያሳያል፡፡ ታዲያ ምን ያደርጋል አልተቻለውም፡፡ ራሱን ጠፍሮ በማሠር ስለማኅበሩ እንዲናገር አሰቃየው እንጂ ስለሌላ ማኅበር እንደሚናገር ተገልጦበታል፡፡ ጸሐፊው ያለ እርሻው የበቀለ ከሌላ ዘር የመጣ ነውና የራሴ ነው ያለውን ማኅበር ”እነርሱ” ”እርሱ” እና ”እኛ” እያለ ጠራው፡፡ ያልሠለጠነ ውሸታም በመሆኑ እንዲጽፍላቸው የቀጠሩትን ሰዎች አጋለጣቸው፡፡ ከእግዚአብሔር ዘንድ ወዴት መሸሸግ ይቻላል? የጨለማው መጋረጃ ተቀደደባቸው፣ ከእነ ተንኮላቸው እጅ ከፈንጅ ተያዙ፡፡ ወዲህና ወዲያ እንዳይሉ በራሳቸው ገመድ ተጠፍንገው ታሠሩ፡፡ እግዚአብሔር ይፍታችሁ ከማለት ውጭ ምን እንላለን?

ማኅበሩ ማኅበሩን ሲቃወም በዕቅዳቸው ውስጥ ማኅበረ ቅዱሳን የሚያሳትማቸውን ኅትመቶች ያለ ኤዲቶሪያል ቦርድ ኅትመት አከናውኖ ማሠራጨት የሚል የተጠላለፈ አሳብ አስቀምጧል፡፡ በመሠረቱ ማኅበረ ቅዱሳን በመዋቅሩ እንዳመለከተው ማንኛውንም ኅትመት ኤዲቶሪያል ቦርዱ ዓይቶት ሲፈቅደው ይታተማል፡፡ ታዲያ እንዴት አንድ ማኅበር የራሱን መዋቅር የጣሰ ለመሥራት ያቅዳል፡፡ አስፈላጊ ሆኖ ካገኘው ቦርዱን ማፍረስ ሲችል እንዴት ስለመጣስ ያስባል። እንዲህ ያለ ዕቅድ ታይቶም ተሰምቶም አያውቅምና ዕቅድ አውጪዎቹ በጣም የተራቀቁ መሆን አለባቸው፡፡ ዕቅዳቸውን ለራሳቸው ጥብቅና ሲያቆሙት ቅድስቲቱን እምነት ለመበረዝ የተነሡ የተሐድሶ ኦርቶዶክስ ዓላማ አራማጆች ስውር ተልኮአቸው በአሁኑ ወቅት ስለተነቃባቸው ከገቡበት አዙሪት ለመውጣት ሲፍጨረጨሩ ይታያሉ፡፡

ከዚህም መንገድ አንዱ ተሐድሶ የሚባል የለም የሚል መፈክራቸውን ማስተጋባት ነው፡፡ ዕቅድ ተብየውም ይህንኑ የተከተለ ሳያውቀው በስውር ዓላማቸው የተቃኘ የተነረተ የበሽታ ሆድ ሆኖባቸዋል፡፡ ስለሆነም ከዕቅዱ መካከል በአንዱ ላይ ታላላቅ የቤተክርስቲያን መሪዎችና ተሐድሶዎች /ፖለቲከኞች/ ናቸው በማለት ከምዕመኑ ሰላማዊ ቅብብል እንዳይኖራቸው የሚል ይገኛል /ቃላቱ እነርሱ እንዳስቀመጧቸው የተቀመጡ ናቸው/። በዚህ ዕቅድ ላይ ሁለት ዋና ዋና ነጥቦችን ማስተዋል እንችላለን፡፡አንደኛው ተሐድሶን ፖለቲከኛነት ጋር ለመቀላቀል መታሰቡ ሲሆን ሁለተኛው ግን ታላላቅ የቤተክርስቲያን መሪዎች ያሏቸውን የሚመለከት ነው፡፡ ተሐድሶ ማለት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲየንን ሙሉ በሙሉ ወደ ፕሮቴስታንት ጐራ ለመክተት አቅዶ የሚሠራ ሲሆን ፖለቲካኛ ደግሞ ሌላ ለዕቅድ አዘጋጆች ግን ተሐድሶና ፖለቲካ ተቀላቅሎባቸዋል፡፡ እውን  ተቀላቅሎባቸው ይሆንን? መልሱ ለአንባቢው የሚተው ነው፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ታላላቅ የቤተክርስቲያኗ መሪዎችን ማኅበረ ቅዱሳን ስማቸውን እንደሚያጠፋ ያመላክታል፡፡ ታላላቆችማ ታላላቆች ናቸው፡፡እነርሱን የሚቃወም ማንነቱ ግልጽ ነው፡፡ ስም ማጥፋትም ወንጀል ነው፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ግን ተሐድሶ የሆኑትን ተሐድሶ ናችሁ ከማለት አስያፈገፍግም፡፡ ይህንን ሲያደርግ በማስረጃ እንጂ በተራ አሉቧልታ አይደለም፡፡ ነገር ግን ታላላቆችን አባቶች የሚነኩትን ማኅበሩም ዝም  አይላቸውም ተልኳቸው ይታወቃልና፡፡ ይሁን እንጂ ሊያስተላልፉ የፈለጉት ተሐድሶ የለም የሚለውን የዘወትር የጨለማ መጋረጃቸውን ለመሆኑ ማን ሁለት ጊዜ ያስባል? ድንጋይ ይቧጥጣሉ እንጂ መጋለጣቸው አይቀርም፡፡ ይህ ሁሉ የሐሰት ደበሎ ይገለጣል፡

የጽንሰ ሐሳብ ችግር

ከዝርዝር ዕቅዳቸው አንዱ ባልተጠኑ ትምህርቶች የቤተርክስቲያኗን ምዕመናን ደጋፊ ማድረግ ይላል። አንድ ጤናማና የሚያስብ አእምሮ ያለው ሰው ይህንን አባባል እንዴት ይረዳዋል? ብሎ መገመት እጅግ ቀላል ይሆናል፡፡ ዕቅድ እያቀደ ያለ አንድ አካል እንዴት ባልተጠና ትምህርት ሌላውን ሊያሳምን ይችላል? ዕቅዱን ያቀዱት ሰዎች የሰለቻቸው ይመስላል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤያት /የከፍተኛ ትምህርት ተቋማትን ተማሪዎችን/ የሚያስተምረው በተጠና ሥርዐተ ትምህርት መሆኑን ያወቁ እንዴት ይህን ሊሉ ቻሉ? በርግጥም ደክሟቸው መሆን አለበት፡፡

የጽሑፉ ዓላማ

 ማኅበረ ቅዱሳን ከተለያዩ የቤተ ክርስቲያን የቁርጥ ቀን ማኅበራትና ልጆች ጋር በመቀናጀት በአሁኑ ሰዓት ፀረ ተሐድሶ እንቅስቃሴ እያደረገ ይገኛል፡፡ በዚህም ምክንያት ማዕበሉ እያንጓለለ የለያቸው ያሉ የተደራጁ  የሃይማኖት ጠላቶች ማምለጫ እስኪያጡ ድረስ አጣብቂኝ ውስጥ ገብተዋል፡፡ የተዋሕዶ ምዕመናንን እየሰለቿቸው መጥተዋል፡፡ በመሸማቀቅ በቁማቸው አልቀዋል፡፡ ከመጠን በላይ በመደንገጣቸው ምክንያት ሳያስቡት የመጣባቸውን እውነት ለመጋፈጥ የሚያስችል መንፈሳዊ ተክለ ሰውነት አጥተዋል፡፡  ስለሆነም አቋራጭ የመሰላቸው የጨነገፈ ስልት ነድፈዋል፡፡ በዋነኛነትም የሞት ሽረት ትግል ለማድረግ አስበዋል፡፡

በዚህም መንገዳቸው አንዱ የማኅበሩን ስም በድብቅ ሆኖ ማጥፋት ነው፡፡ እውነተኞች ሰዎች ከሆኑ ማንነታቸውን ገልጠው ፊት ለፊት በያዙት መረጃ በታገሉ ነበር፡፡ ለዚህ ያልታደሉ የመልካም ዘር ፀሮች በመሆናቸው መደበቁን መርጠዋል፡፡ ተደብቆ ውጭ ማኅበረ ቅዱሳን ሊያስበው ከቶውኑ የማይፈልገውን ያስቡለታል፡ ፡ “አዛኝ ቅቤ አንጓች” እንደሚባለው ሆኖባቸው በዚህ ስልት ማኅበሩን ለማጥቃት ሞክረዋል ራሳቸው ጽፈው ሊሰሙን ይችላሉ ብለው ለሚያስቧቸው አካላት ጽሑፉን ለመበተን ሞክረዋል፤ ይህንን ማድረጋቸውም አንድም አባቶችን ንቀዋቸዋል አለበለዚያም ተዳፍረዋል፡፡

ይህንን ከደረጃ ወጥቶ ጊዜ ወስዶ የተንኮታኮተ ጽሑፍ ዕቅድ ብለው ይዘው መዞራቸው በትክክል ማንነታቸውን ይገልጥባቸዋል፡፡ በየትኛውም መመዘኛ ማኅበረ ቅዱሳንን የማይመስል ወዘና የሌለው ወረቀት ብቅ ማድረግ ማንነታቸውን ገልጠዋል፡፡ በዝምታ ሊታለፉ አይገባቸውም፡፡

ማጠቃለያ
ይህንን ጽሑፍ ያሰራጩት አካለት እነማን ሊሆኑ እንደሚችሉ ማንም ሰው መገመት ይችላል፡፡ ከመገመትም አልፎ አገኘሁ ብሎ ማኅበሩን ለማጥላላት የሚጠቀምበት ሁሉ እንዳለ ይታወቃል፡፡ ተቀባዮችም የሰጪዎችን ማንነት ያውቃሉ፡፡ እንዲያውም ከማብራሪያ ጋር እንደተቀበሉ ይታመናል ፡፡

ስለሆነም፡-

1. ይህ የሐሰት ጽሑፍ የደረሳቸው አካላት ሰዎችን በማጋለጥ ሊተባበሩ ይገባል፤
2. ማኅበሩ እነዚህን አካላት በሕግ መጠየቅ ይፈልጋል፡፡ ስለሆነም ቅዱስ ሲኖዶስ የእነዚህን ሰዎች ማንነት አጣርቶ ፍትሐዊ ውሳኔ እንዲሰጥን እንፈልጋለን፤

3. ይህ ጽሑፍ የደረሳቸሁ ምዕመናን በሐሰት ሥራ እንዳትታለሉ እናሳስባለን። አስፈላጊ ሆኖ ካገኙትም ወደ ማኅበሩ ጽ/ቤት በመምጣት ተገቢውን ውይይት ማድረግ እንደሚችሉ እንጠቁማለን።

የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ ዛሬ ተጀመረ፡፡

ግንቦት 10፣ 2003ዓ.ም


በርክበ ካህናት የሚደረገው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ ዛሬ ተጀመረ። ጉባኤውን ተከትሎ የተለያዩ እንቅስቃሴዎች እየተደረጉ ነው፡፡

 
ወደ 1000 የሚጠጉ የሐዋሳ ከተማ ምዕመናን አዲስ የተመደቡትን የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ካህናት ጌታቸው ዶኒን ሹመት በመቃወም በሀገረ ስብከታቸው የተፈጠሩ ችግሮች የመጨረሻ እልባት እንዲሰጥበት የተለያዩ መፈክሮችን በመያዝ በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅድሳን ማረያም ገዳም በመገኘት አቤቱታቸውን አቅርበዋል፡፡  ከቅዱስ ሲኖዶስ መክፈቻ ጸሎት በኋላ ለቅዱስነታቸው እና ለብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ጥያቄያቸውን ያቀረቡት ምዕመናኑ «በምልዐተ ጉባኤው አጀንዳ ተደርጎ ሊያዝ እንደሚችል ቃል ተገብቶልናል» ሲሉ በቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ለተሰበሰበው ምእመን በተወካያቸው አማካይነት ገልጸዋል፡፡

ከሓዋሳ የመጡ ምእመናን አስፈላጊውን የሕግ አግባብነት ተከትለው ቢመጡም ባልታወቀ ምክንያት ዱከም ላይ ታግተው የቀሩ ምእመናን እንዳሉ አስተባባሪዎች ገልጸዋል፡፡

በሰ/ት/ቤቶች ማ/መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳንም የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ በአጀንዳ ሊያያቸው ይገባል ያላቸውን ጉዳዮች በቀን 9/9/03 ዓ.ም በቁጥር ማ.ቅ.ሥ.እ.መ/17/02/ለ/03 በጻፈው ደብዳቤ አቅርቧል፡፡ ለቅዱስ ሲኖዶስ ጽሕፈት ቤት እና በግለባጭ ለሁሉም ሊቃነ ጳጳሳት በላከው ደብዳቤ በማኅበሩ ላለፉት 19 ዓመታት የተሠሩ ሥራዎች እንዳሉ ሆነው በአሁኑ ወቅት ግን ለቤተ ክርሰቲያን እድገትና መልካም አሠራር እንቅፋት የሆኑ ችግሮች  መኖራቸውን በአጽንኦት ይገልጻል፡፡

ወቅታዊውን የተሐድሶ መናፍቃን ዘመቻ፣ ቅዱስ ሲኖዶስ ከዚህ በፊት ያሣለፋቸውን ውሳኔዎች ተፈጻሚነትን፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ትውልድን የማፍራት ጉዳይ ይኸውም የሕፃናትና የወጣቶች ሰ/ት/ቤቶች ሥርዓተ ትምህርትና የማደራጃ መምሪያ ኃላፊዎችን ችላ ባይነት፣ የማኅበሩን ስም ለማጥፋት እየተንቀሳቀሱ ስላሉ አጽራረ ቤተ ክርስቲያን እንዲሁም ለቅዱስ ሲኖዶስ አባልነትና የሚቀርቡና የሚሾሙ ኤጲስ ቆጶሳትን ጉዳይ ይኸውም ወቅቱ የተሐድሶ መናፍቃን በቤተ ክርስቲያኗ መዋቅርና የሓላፊነት ቦታ ለመግባት ከፍተኛ ርብርብ የሚያደርጉበት ስለሆነ ቅዱስ ሲኖዶስ ለዚህ ጉዳይ ጥንቃቄ እንዲያደርግ የሚያመለክቱ አጀንዳዎች በአጀንዳነት ተይዘው ውሳኔ ሊሰጥባቸው ይገባል በማለት እንደልጅነታችን ሀሳባችንን እናቀርባለን ሲል ለቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት የተጻፈው ደብዳቤ ያሳስባል።


 


በተያያዘም እነዚህንና ከወቅቱ ሁኔታ ጋር የቀረቡ ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮችን በተመለከተ በወቅታዊው የስምዐ ጽድቅ ልዩ እትም ሠፋ ያሉ ዘገባዎች ቀርበዋል።

ቅዱስ ሲኖዶስንና መንፈሳዊና አስተዳደራዊ ልዕልናውን፣ የወቅታዊውን የተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴ፣ እንዲሁም አጽራረ ቤተ ክርስቲያን፣ በማኅበረ ቅዱሳን የውሸት /forged/ ማኅተም «የማኅበረ ቅዱሳን የረጅም ጊዜ ዕቅድ» በሚል ያዘጋጁትን እና በክስ መልክ ለፓትርያኩ ያቀረቡትን የሐሰት ጦማርና ሌሎችንም ወቅታዊ ጉዳዮች በተመለከተ ሰፋ ያለ ዘገባ በመያዝ ወጥታለች፤ የስምዐ ጽድቅ ልዩ እትም።

ቤተ ክርስቲያን የማትነጥፍ መንፈሳዊት ጥገት ሆና ከምታፈሰው መንፈሳዊ ሐሊብ /ወተት/ ምእመኖቿ እንዲጠቀሙ የቅዱስ ሲኖዶስ መንፈሳዊና አስተዳደራዊ ልዕልና መከበር ወሳኝ ነው።

ቤተ ክርስቲያንም የቅድስና ዘውዷንና የክብር አክሊሏን ከራሷ ሳታወርድ ልዕልናዋ እንዳለ ሁሉ የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች መከበር አለባቸው ስትል ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ በልዩ እትሟ አስነብባለች።