ሰሙነ ሕማማት ( ዘሰሉስ)

ማክሰኞ

በዚህ ዕለት ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱሱ ክርስቶስ ስለ ሥልጣኑ ተጠይቋል፡፡ ጠያቂዎቹ የካህናት አለቆችና የሕዝብ አለቆች ናቸው፡፡ ጥያቄውም በማን ሥልጣን እነዚህን ታደርጋለህ? ይህንስ ሥልጣን የሰጠህ ማነው?€ የሚል ነበር፡፡ የካህናት አለቆች ያቀረቡት ጥያቄ ነበር፡፡ ጌታችን ሰኞ ዕለት ሁለት ነገሮችን ማድረጉን ተያይዞ የተነሣ ጥያቄ ነው፡፡ ሰኞ ከቅጠል ብቻ በቀር ፍሬ ያላገኘባትን ዕፀ በለስ ረግሟል፤ በማስከተል ወደ ቤተ መቅደስ ገብቶ የሚሸጡትንና የሚለውጡትን አስወጥቷል፡፡ ማቴ.21:23-25፤ ማር.11:27፣ ሉቃ.20·1-8፡፡ ከላይ እንደ ተገለጸው ጌታችን ሲያደርጋቸው የነበሩት ተአምራትና የኃይል ሥራዎች የካህናት አለቆችን ስላስቀናቸው ጌታችንን ከሮማ መንግሥት ባለ ሥልጣናት ጋር ለማጋጨት የቀየሱት ስልት ነው፡፡

ጌታችን በቤተ መቅደስ የነበሩትን ነጋዴዎችን አባሯል፤ መደባቸውን ገለባብጧል፡፡ ነጋዴን ማባረርና መደብን ማስለቀቅ መንግሥታዊ ሥራ ነው፡፡ በአንድ አገር የንግድ ቦታን የሚያጸድቅ መንግሥት መሆኑ እሙን ነው፡፡ ጌታችን ፈሪሳውያን ላቀረቡት ጥያቄ ቀጥተኛ መልስ አልመለሰም፡፡ ምክንያቱም ጥያቄው ለከሳሾቹ አመቺ ሁኔታን ስለሚፈጥር ጥያቄውን በጥያቄ መልሷል፡፡ በመባሕተ መኑ ትገብር ዘንተ፤ በማን ሥልጣን ነው ይህን የምታደርገው? ነበር ያሉት፡፡ በራሴ ሥልጣን ቢላቸው ፀረ መንግሥት አቋም አለው በማለት ከሮማ መንግሥት ዘንድ ለማሳጣት ነበር ዕቅዳቸው፡፡

ጌታችን እኩይ የሆነውን የፈሪሳውያንን አሳብ በመረዳት œየዮሐንስ ጥምቀት ከየት ነው ከሰማይ ነው ወይስ ከምድር ሲል ጠይቋቸዋል፡፡ ከሰማይ ያልነው እንደ ሆነ ለምን አላመናችሁበትም ይለናል:ከሰው ያልነው ከሆነ ሕዝቡ ይጣላናል፡፡ ምክንያቱም ሕዝቡ ዮሐንስን እንደ አባት ይፈሩት እንደ መምህር ያከብሩት ነበርና ሕዝቡን እንፈራለን ተባብለው ከወዴት እንደሆነ አናውቅም ብለው መለሱለት፡፡ እርሱም እኔም በማን ሥልጣን እነዚህን እንደማደርግ አልነግራችሁም አላቸው፡፡ ይህንንም መጠየቃቸው እርሱ የሚያደርጋቸውን ሁሉ በራሱ ሥልጣን እንዲያደርግ አተውት አልነበረም፣ ልቡናቸው በክፋና በጥርር ስለተሞላ እንጂ፡፡ 

በማቴ.21፡28፤ 25፡46፤ ማር.12፡2፤ 13፡37፤ ሉቃ.20፡9፤ 21፡38 የሚገኙት ትምህርቶች ሁሉም የማክሰ ትምህርት ባላሉ፡፡ በዚህ ዕለት በቤተ መቅደስ ረጅም ትምህርት ስላስተማረ የትምህርት ቀንም ባላል፡፡ ክርስቲን የሆነ ሁሉ ከሥጋዊ ነገር ርቆ በዚህ ሰሞን የሃማኖት ትምህርት ሲማር ሲይቅ መሰንበቱ መጽሐፋዊ ሥርዓት ነው፡፡

ዛሬም ቢሆን መልካም ሥራን በሠራን ጊዜ ከልዩ ልዩ ወገኖች የሚመጡ ፈተናዎች ለመልካም ሥራችን እንቅፋት ሊሆን እንደሚችሉ መገንዘብ አለብን፡፡ ብዙ ወገኖች ለቅን አሳባችን ለምን ሰዎች ክፉ ነገር ይመልሱልናል በማለት ሲጠይቁ ይሰማል፡፡ ለቅን ዐሳባችን ከዓለም ዘንድ የተገላቢጦሽ ነገር እንደ ሚጠብቀን ዓለም የሚወደው የገዛ ወገኑን ነው የሚለውን የጌታችንን ትምህርት ልብ ይሏል፡፡ ይህ በመሆኑ በዘመናችን አሳልፈው ሊሰጡን የሚፈልጉ ሰዎች ፈታኝ ጥያቄ እንደሚያቀርቡልን ከወዲሁ ልንገነዘብ ይገባል፡፡

ሰሙነ ሕማማት

ሚያዝያ 1/2004 ዓ.ም. 

መምህር ኃይለ ማርያም ላቀው

ፍቅር የተከፈለ የመሥዋዕትነት ሥራ ስለ ተሠራበት፣ የሰው ልጆች ደኅንነት ስለ ተፈጸመበት፣ መድኀኔዓለም ስለ እኛ ቤዛ ሆኖ ለመስቀል ሞት ታዛዥ ሆኖ ነፍሱን ስለ ካሠልን “ቅዱስ ሳምንት” ተብሏል፡፡ በተጨማሪም “የመጨረሻ ሳምንት” ተብሎ ይጠራል፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ዓለም በሙዓለ ሥጋዌው ለፈጸማቸው የቤዛነትና የአርአያነት ተግባራት ፍጻሜ በመሆኑ ነው፡፡

በዚህ ልዩ በሆነ ሳምንት ካህናትና ምእመናን በነግህ፣ በሠልስት፣ በቀትር፣ በተሰዓትና በሠርክ ወደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በመጓዝ ስለ ጌታችን ኢየስስ ክርስቶስ ሕማማተ መስቀል የሚያዘክረውን ምዕራፍ ከቅዱሳት መጻሕፍት በማንበብና በመጸለይ ሕማሙንና ሞቱን ያዘክራሉ፤ ቅዱስ ያሬድ በመጨረሻው ሳምንት በየዕለቱ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ላይ የተፈጸመውን ነገረ መስቀል በተመለከተ ያዘጋጀውን መዝሙር ይዘምራሉ፤ አብዝተው ስግደትን ይሰግዳሉ፡፡

 

ሰሙነ ሕማማትን ከሌሎች የዐቢይ ጾም ሳምንታት ልዩ የሚያደርገው ሥርዓት አለ፡፡ በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት ሥርዓትና ደንብ መሠረት በሰሙነ ሕማማት ከጸሎተ ሐሙስ በስተቀር ቅዳሴ አይቀደስም፣ ስብሐተ ነግህ አይደረስም፣ ጸሎተ ፍትሐት አይጸለይም፣ ጸሎተ አስተስርዮም አይደረግም፡፡ እንዲሁም ጥምቀተ ክርስትናም አይፈጸምም፡፡ ከላይ የተዘረዘሩት የቤተ ክርስቲያን ሥርዓቶች አስቀድሞ በዕለተ ሆሳዕና ይከናወናሉ፡፡

 

በተጨማሪም ማንኛውም ክብረ በዓል በዚህ ሳምንት ቢውል ከትንሣኤ በኋላ እንዲከበር ይተላለፋል፡፡ ይህ ብያኔ በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት ዘንድ የጸና ኦርቶዶክሳዊ ሥርዓት ነው፡፡ ሕማምና ሞት የማይገባው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የእኛን ሕማምና ሞት ለራሱ በማድረግ በዚህ ሳምንት ለእኛ ቤዛ ሆኗል፡፡ “ደዌያችንን ተቀበለ፤ ሕማማችንንም ተሸከመ፤ ከዓመፀኞችም ጋር ተቆጠረ፡፡ እርሱ ግን ግፍን አላደረገም ተንኮልም በአፉ አልተገኘበትም፡፡” /ኢሳ.53÷4-12/ ተብሎ እንደ ተጻፈ፡፡ ምእመናን ክርስቶስ የተቀበለው የእኛን ሕማም መሆኑን በማዘከር በሰሙነ ሕማማት ከማንኛውም የሥጋ ሥራ መታቀብ ዋዛ ፈዛዛ ባለመነጋገር በኀዘን ልናከብረው ይገባል፤ ብድራትን የማያስቀረው አምላክም መተላለፋችንና በደላችንን በመደምሰስ የመንግሥቱ ወራሽ ያደርገናልና፡፡

 

ሰሙነ ሕማማት አስከ አራተኛው ምዕተ ዓመት ድረስ ከጾሙ ተለይቶ ለብቻው ይከበር ነበር፡፡ በኋላ ግን በባሕረ ሐሳብ ቀመር መሠረት ጾሙም ሕማማቱም ትንሣኤውም ተያይዘው እንዲከበሩ ተደረገ፡፡ ምዕራባውያን ከአርባ ጾም ውስጥ የመጨረሻውን ሳምንት ሰሙነ ሕማማት ያደርጉታል፡፡ የምሥራቃውያን /ኦሪየንታል/ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት ግን አርባውን ጾም ጨርሰን ከኒቆዲሞስ በኋላ ያለውን ተከታዩን አንድ ሳምንት ሰሙነ ሕማማት አድርገን እናከብራለን፡፡ከእነዚህ የሕማማት ሳምንት ውስጥ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሦስቱ ዕለታት /በሰኞ፣ ማክሰኞ እና ረቡዕ/ ያከናወናቸው የድኅነት ሥራዎች የሚከተሉት ናቸው፡፡

 

ሰኞ

ጌታችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው ሆኖ በዚህ ዓለም ሲመላለስ በሆሳዕና ማግሥት ጌታችን ከቢታንያ ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባ ሁለት ነገሮችን አድርጓል፡፡ አንደኛ ከቅጠል በስተቀር ፍሬ ያልተገኘባትን ዕፀ በለስ ረግሟል፡፡ ሁለተኛ ወደ ቤተ መቅደስ ገብቶ የሚሸጡትንና የሚለውጡትን አስወጥቷል፡፡/ማቴ.21÷12-17፤ ማር.11÷17፤ ሉቃ.19÷45-46፡፡/ በቅዱስ ማቴዎስ አገላለጥ “በማግሥቱ ተራበ” የሚል ቃል እንመለከታለን፡፡

 

ነቢዩ ኢሳይያስ “እግዚአብሔር ለዘለዓለም አይራብም፤ አይጠማም፤ አይደክምም” /ኢሳ.46÷25/ ይላል፡፡ በቅዱስ ወንጌልም “በመጀመሪያ ቃል ነበር” ይላል፡፡ ያ ቃል ቀዳማዊ እንደ ሆነ፣ ቃል በእግዚአብሔር ዘንድ እንደ ነበር፣ ያም ቃል እግዚአብሔር ነው ተብሎ ተጽፏል፡፡ ዮሐ.1÷1-2፡፡ ጌታችንም በመዋዕለ ትምህርቱም ሲያስተምር “የእኔስ መብል የላከኝን የአባቴን ፈቃድ አደርግ ዘንድ፡ ሥራውንም እንፈጽም ዘንድ ነው” /ዮሐ.4÷34/ ሲል ተናግሯል፡፡ ነቢዩ እግዚአብሔር እንደማይራብ ተናግሯል፡፡ ታዲያ ጌታችን ለምን ተራበ?

 

ሰማያውያን መላእክት እንዳይራቡ አድርጎ የፈጠረ፣ እስራኤልን ገበሬ በማያርስበት፣ ዘር በሌለበት፡ ዝናብ በማይጥልበት ምድረ በዳ የመገበ ፤ድኅረ ሥጋዌ በአምስት አንጀራና በሁለት ዓሣ ከ5000 የሚበልጡ ሰዎችን የመገበ ተራበ! ተብሎ ሲነገር እጅግ ይደንቃል፡፡ በእርግጥ ፍጹም አምላክ ፍጹም ሰው በመሆኑ አልተራበም አንልም፡፡ የጌታችን ረሃብ ንዴት ያለበትና የአንዲት የበለስ ዘለላ ረሃብ አይደለም፡፡ ረሃቡ የበለስ ፍሬ ሳይሆን “በለስ ብሂል ቤተ እስራኤል እሙንቱ” እንዲል የሃይማኖትና የመልካም ሥነ ምግባርን ፍሬ የሻ መሆኑን ለማጠየቅ ነው፡፡ ጌታችን የፈለገውን ባለማግኘቱ ጉባኤ አይሁድን ረግሟል፡፡ በአይሁድ ጉባኤ የነገሠውን ኃጢአት፤ በበለስ አንጻር መርገሙን ታላቁ ሊቅ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ “በአንጻረ በለስ ረገማት ለኃጢአት፤በበለስ አንጻር ኃጢአትን ረገማት” ብሏል፡፡

 

እስራኤልም በአንድ ወገን የተጠበቀባቸውን ፍሬ ባለማፍራታቸው ተረግመዋል፡፡ ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እስራኤል ከፍቅር ይልቅ እርግማን እንዳገኛቸው አሕዛብ ደግሞ የቃሉን ትምህርት ሰምተው የእጁን ተአምራት አይተው የአመኑበትን የእግዚአብሔር የጸጋ ልጁ ለመሆን መብቃታቸውን ሲመሰክር እንዲህ ይላል፡- “አሕዛብ አስተጋብኡ ጽጌሬዳ በኂሩቱ ወሶኩሰ ተርፈ ኀበ አይሁድ ዘውእቱ ሕፀተ ሃይማኖት፤ አሕዛብ በእግዚአብሔር ቸርነት አበባ ሰበሰቡ፤ በአይሁድ ዘንድ ግን እሾኹ ተረፈ፡፡ ይኽውም የሃይማኖት ጉድለት ነው፡፡” ብሎ ተርጉሞታል፡፡ እሾኽ የእርግማን ምሳሌ ነው፤ አበባ የእግዚአብሔር ጸጋ ልጅነት ምሳሌ ነው፡፡ ዛሬ የእግዚአብሔር ቤተሰቦች ጌታችን ወደ መቅደስ ሕይወታችን ቢመጣ ምን ያገኝ ይሆን? ፍሬ ወይስ ቅጠል? የእግዚአብሔር ቃል ግን ለንስሐ የሚገባ ፍሬ አድርጉ ይለናል፡፡ ማቴ.3÷8፡፡ ስለዚህ እግዚአብሔር ከእኛ የሚፈልገውን የመንፈስ ቅዱስ ፍሬ እናፍራ፡፡ ገላ.5÷22፡፡ ጌታችን በዳግም ልደት ሲመጣ ከሰው ልጅ ሃይማኖት መገኘቱ አጠራጣሪ እንደሆነ ተናግሯል፡፡ “የሰው ልጅ ወደዚህ ዓለም ሲመጣ ሃይማኖት ያገኝ ይሆንን?” ቀጣይ ሕይወታችንን በአምላካዊ ሥልጣኑ የቃኘ አምላክ በመጣ ጊዜ የእምነት ፍሬ አፍርተን ከእግዚአብሔር ዘንድ ዘላለማዊ ፍቅሩን ለማትረፍ እንትጋ፡፡

የቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያንን ዳግም ለማነጽ የገቢ ማሰባሰቢያ ተካሔደ

መጋቢት 28/2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

በቅርቡ በአክራሪ ሙስሊሞች ሙሉ ለሙሉ ወደተቃጠለው በስልጤና ሃዲያ፣ ጉራጌ ከንባታ ሀገረ ስብከት ጋራሬ ቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያን መጋቢት 23/2004 ዓ.ም. መንፈሳዊ ጉዞ ተካሔደ፡፡ የጉዞው ዓላማ በቃጠሎው ምክንያት የተጎዱትንና ተስፋ በመቁረጥ ላይ የሚገኙትን የአካባቢውን ምእመናንን በቃለ እግዚአብሔር ለማጽናናት ቤተ ክርስቲያኑን ዳግም ለማነጽ እንዲረዳ የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር ለማካሔድ ታስቦ የተዘጋጀ ነበር፡፡

አዲስ አበባ በሚገኘው በማኅበረ ነህምያ የስልጤ ዞን አብያተ ክርስቲያናት መርጃ ማኅበር ከሥልጤ አካባቢ ተወላጆች ጋር በመተባበር የተዘጋጀ ጉዞ ሲሆን በተጨማሪም በአዋሳና ሻሸመኔ የሚገኙ ምእመናን ቤተ ክርስቲያኗ ያለችበት ሁኔታ ለማየትና የአቅማቸውን አስተዋጽኦ ለማድረግ በቦታው ተገኝተዋል፡፡

 

በሥፍራው ከተገኘው ማኅበረ ምእመናን በተደረገው የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር በጥሬ ገንዘብ ከ200,000 /ሁለት መቶ ሺህ ብር/ በላይ ሊሰበሰብ ችሏል፡፡ በተጨማሪም ገንዘብና ጥሬ እቃ ለማቅረብ ከምእመናን ቃል የተገባ ሲሆን በዕለቱ በተጋበዙ መምህራነ ወንጌል የማጽናኛ ትምህርት የተሰጠ ሲሆን ያሬዳዊ ዝማሬም ቀርቧል፡፡

 

ከሥፍራው ያገኘነው መረጃ እንደሚጠቁመው ከመንግሥት በተሰጠው ውሳኔ መሠረት ቤተ ክርስቲያኑን ለመሥራት ተለዋጭ ቦታ የተሰጠ ሲሆን የይዞታ ማረጋገጫም ለማግኘት ተችሏል፡፡ የቀድሞው ቤተ ክርስቲያን ይዞታ አሁን ከተሰጠው ቦታ ድንበር ላይ የሚገኝ ሲሆን ለጥምቀተ ባህር ቤተ ክርስቲያን  እንድትጠቀምበት ውሳኔ አግኝቷል፡፡

 

የአካባቢው ምእመናን ከጎናቸው መሆናቸውን ለመግለጽና ለማጽናናት የመጡትን ምእመናን አመስግነው በተካሔደው መርሐ ግብር እንደተደሰቱ በመግለጽ ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡ በዕለቱ ከ1500 በላይ ምእመናን በመርሐ ግብሩ ላይ ተሳትፈዋል፡፡

 

የጋራሬ ቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያንን ዳግም ለማነጽ ግንቦት 5/2004 ዓ.ም. የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ አቡነ ቀሌምንጦስ  የመሠረት ድንጋይ ያኖራሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡

ከ175 በላይ በገና ደርዳሪዎች ይመርቃሉ፡፡

መጋቢት 26/2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደጀኔ

በማኅበረ ቅዱሳን ልማት ተቋማት አስተዳደር የአቡነ ጎርጎርዮስ የትምህርትና ሥልጠና ማእከል ከ175 በላይ በገና ደርዳሪዎችን መጋቢት 29 ቀን 2004 ዓ.ም. እንደሚያስመርቅ አስታወቀ፡፡

የትምህርትና ሥልጠና ማእከሉ ሓላፊ አቶ አብዮት እሸቱ እንደገለጹት ማኅበረ ቅዱሳን ከዚህ በፊት በዜማ ማሠልጠኛ ክፍሉ በርካታ በገና ደርዳሪዎችን ማስመረቁን ገልጸው የአሁኖቹን ተመራቂ ጨምሮ ከ1200 በላይ በገና ደርዳሪዎቹን በማእከሉ ማሠልጠኑን ገልጸዋል፡፡

 

መጋቢት 29 ቀን 2004 ዓ.ም. በጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ ከቀኑ 7፡30 በሚካሔደው የምረቃ መርሐ ግብር ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የተመራቂ ቤተሰቦችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች እንደሚገኙ የገለጹት የማእከሉ ሓላፊ ማኅበረ ቅዱሳን ቅዱስ ሲኖዶስ በሰጠው መተዳደሪያ ደንብ መሠረት የቤተ ክርስቲያንን እምነት፣ ሥርዐት፣ ትውፊትና ዶግማ ተጠብቆ ወደ ቀጣዩ ትውልድ ለማስተላለፍ የተሰጠውን ሓላፊነት እየተወጣ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

 

የአቡነ ጎርጎርዮስ የትምህርትና ሥልጠና ማእከል በአሁኑ ወቅት ከ KG እስከ 9ኛ ክፍል ተማሪዎችን በቀለም ትምህርት እያስተማረ የሚገኝ ሲሆን በዜማና በአብነት የትምህርት መስክ ሥልጠናዎችን እየሰጠ እንደሚገኝ አቶ አብዮት ገልጸዋል፡፡

የዐብይ ጾም ስብከት /ክፍል 7/

መጋቢት 26/2004ዓ.ም.

በአያሌው ዘኢየሱስ


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤


ብፁዕ አቡነ መልከ ጼዴቅ የከምባታ፣ ሀድያ፣ ጉራጌና ስልጢ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤በአዲስ አበባ የደብረ ብሥራት ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን የበላይ ኃላፊ፤ቀደም ሲል በዚሁ ደብር አስተዳዳሪ ሆነው ባገለገሉባቸው ዓመታት ውስጥ ለማጠቃለያ ከሰበኳቸው በርካታ የወንጌል ስብከቶች መካከል የተወሰደ፡፡/መጋቢት 21 ቀን 1985 ዓ.ም./

እውነት እውነት እልሃለሁ፡- ሰው ዳግመኛ ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ የእግዚአብሔርን መንግሥት አያይም፡፡ ጌታችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይህንን የተናገረው ለኒቆዲሞስ ነው፡፡

ኒቆዲሞስ የሃይማኖት ሊቅ ነው፡፡ ብዙ የተማረ ብዙ ያወቀ ሰው ነው፡፡ ከዚህም የተነሣ ሊቅ – ምሁር – አለቃ ተብሎ ተጠርቶአል፡፡ በጊዜው ከነበሩ ሰዎች ከፍ ያለና የላቀ ዕውቀት የነበረው ሰው ነበር፡፡ በሌሊት ወደ ጌታ እየመጣ ይማር ነበር፡፡ የማታ ተማሪ ነበር፡፡ ቀን – ቀን የምኩራብ አስተማሪ ሆኖ ብዙ ሰዎችን ያስተምር ስለ ነበረና እርሱ የሚያስተምራቸው አይሁድ ጌታን ስላልተቀበሉ ቀን ለቀን መጥቶ የሚማርበት አመቺ ጊዜ አልነበረውም፡፡

በአይሁድ ሕግ ጌታን የሚከተልና የሚቀበል ሰው ከምኲራብ የሚባረር ስለሆነ እነርሱን ላላማስቀየም ማታ ነበር የሚማረው፡፡ ኒቆዲሞስ ለጌታ ከሰው ችሎታ በላይ የሆኑ ተአምራትን ስለምትሠራ እኛን ለማስተማርና ለመምከር ከእግዚአብሔር ዘንድ ተልከህ የመጣህ ነህ ብሎ መስክሮለታል፡፡ ጌታም ለእናንተ ተልኬ የመጣሁ ከሆነና እናንተን ለማስተማር እንደ መጣሁ ከተረዳህ ሰው ዳግመኛ ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት አይገባም አለው፡፡

ኒቆዲሞስ ስላልገባው እኔ አርጅቼአለሁ፤ እንዴት ነው ወደ እናቴ ማኅጸን ተመልሼ የምገባውና ዳግም የምወለደው? ብሎ ኢየሱስ ክርስቶስን ጠየቀው፡፡ ጌታም፡- ሰው ከሰው ከተወለደ ሥጋዊ ነው፤ የሰው ልጅ ነው፡፡ የእግዚአብሔር ልጅ ለመሆን በመንፈስ መወለድ አለበት፡፡ ከእግዚአብሔር መወለድ ነፋስ ከየት ተነሥቶ ወዴት እንደሚነፍስ እንደማይታወቅ ያለ ረቂቅ ምሥጢር ነው አለው፡፡ አሁንም ያ ሊቅ፤ ያ አዋቂ አልገባኝም አለ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስም፡- አንተ የእስራኤል ሊቅና አዋቂ ሆነህ እንዴት ይህን አታውቅም አለው፡፡ ከሰማይ ከወረደው በቀር ወደ ሰማይ የሚወጣ የለም፤ የምናውቀውንም እንናገራለን ካለው በኋላ ጥያቄውን በዚህ ገታ፡፡

ኒቆዲሞስ  ወደ ጌታችን ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ መጥቶ መማሩ የምያስመሰግነው ተግባር ነው፡፡ አይሁድ ወገኖቹ ጌታን ሳይከተሉት እርሱ ጌታን መውደዱ የሚያስደንቅ ነው፡፡ ኒቆዲሞስ የሚያመሸው ከጌታ ጋር ነበር፡፡ ባለችው ትርፍ ጊዜው ሁሉ ወደ ፈጣሪው ይሔድ ነበር፡፡ ይህ ታላቅ ዕድል ነው፡፡ ቀን ሲያስተምርና ሲደክም ስለሚውል ማታ – ማታ ማረፍ ይገባው ነበር፡፡ ኒቆዲሞስ ግን ቤቴ ገብቼ ልረፍ አላለም፡፡ ባለ ሥልጣንና ባለጸጋ ስለ ነበር ደጅ የሚጠናው ሕዝብና መሰል ባልንጀሮቹ ይፈልጉት ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ከእነርሱ ጋር አላመሸም፡፡

ከዚህ አባት ታላቅ ትምህርት ልንማር ያስፈልጋል፡፡ እኛ ዛሬ የምናመሸው የት ነው? የምናመሸውስ ከማን ጋር ነው? ምን ስናደርግ ነው የምናመሸው? ኒቆዲሞስ ቤቱ አልነበረም የሚያመሸው፤  ከእውነተኛው መምህር ጋር እንጂ፡፡ ኒቆዲሞስ ጽድቁንና በረከቱን እየያዘ ነበር ወደ ቤቱ ይገባ የነበረው፡፡ እኛ ወደ ቤታችን የምንገባው እየከበርን ነው ወይ? ጸድቀን ነው የምንገባው ወይስ ጎስቁለን?

የዛሬው ሰው እየሰከረ፣ እየጨፈረ፣ እየደማ፣ እየቆሰለ አብዶ ነው የሚመለሰው፡፡ በቤት ያሉትም እንቅፋት ያገኘው ይሆን? ይሞት ይሁን? እያሉ እየተሳቀቁ ነው የሚያመሹት፡፡ የሚሞትም አለ፡፡ ማምሸት እንደ ኒቆዲሞስ ከጌታ ጋር ነው እንጂ! ኒቆዲሞስ ከጌታ ጋር በማምሸቱ ፈጣሪውን አወቀ፡፡ ጌታን ማወቅ ብቻ ደግሞ አይበቃም፡፡ ማወቅማ አጋንንትም ያውቁታል፡፡ ከመንፈስ መወለድ መወለድ ያስፈልጋል፡፡

ሰው ዕፀ በለስን በበላ ጊዜ የእግዚአብሔር ልጅነቱን ተነጥቆ ነበር፡፡ ጌታ መጥቶ ዳግም ሰው እስከሚያደርገን ድረስ የሰይጣል ልጆች ሆነን ነበር፡፡ ከዚያም በአርባና በሰማኒያ ቀን ከአብራከ መንፈስ ቅዱስና ከማኅፀነ ዮርዳኖስ ተወልደናል፡፡ አባታችን የምንለው ለዚህ ነው፡፡ ከእርሱ ከተወለድንና ልጅነትን ካገኘን እንደገና ልጅነታችንን ካገኘን እንደገና ልጅነታችንን እንዳናጣ አክብረን እንያዘው፡፡ መጀመሪያም አላወቅንበትም ነበር፡፡ አዳም ከገነት የሚወጣ አልመሰለውም ነበር፡፡ ሰይጣን አታሎታል፡፡ እኛም እንደገና እንዳንታለል ልጅነታችን እንዳይሰረዝ እንጠንቀቅ፡፡

የብዙዎቻችን ልጅነት ዛሬ እየተወሰደ ነው፡፡ ልጅነታችንን እያስነጠቅነው ነው፡፡ እነ ኤሳው እየነጠቁን ነው፡፡ ብዙዎች እንደ ያዕቆብ ልጅነታችንን ሊወስዱብን አሰፍስፈዋል፡፡ ሰይጣን እንደ አዳም ሊነጥቀን አሰፍስፏል፡፡ ዛሬ በጣም አርጅተናል፡፡ ኒቆዲሞስ አርጅቶ ነበር፡፡ በጥምቀትና በንስሓ ግን አዲስ ሕይወት አግኝቶአል፤ ታድሷል፡፡ ያረጀው ሕይወቱ ለመለመ፡፡ ያረጀው ሰውነታችንን በሥጋውና በደሙ በንስሓ እናድሰው፡፡ ይህ ከሆነ ነው የእግዚአብሔርን መንግሥት የምንወርሰው፡፡

 

 

baba shenouda

‹‹ትእዛዝህ ከጠላቶቼ ይልቅ አስተዋይ አደረገኝ›› መዝ 118፥98 ፤ በእንተ ቅዱስነታቸው አቡነ ሲኖዳ

መጋቢት 25/2004 ዓ.ም.

በአያሌው ዘኢየሱስ


/ይህ ጽሑፍ ካይሮ በሚገኘው የአሜሪካ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ ፕሮፌሰር የሆኑት ዶክተር አቶ ሜናርደስ “የግብጽ የሁለት ሺህ ዓመት ክርስትና” በሚል ርዕስ ካዘጋጁት መጽሐፍ የተወሰደ ሲሆን የጽሑፍን የአርትኦት ሥራ ያከናወኑት አባ አውጉስጢኖስ ሐና ናቸው፡፡ የዘመን አቆጣጠሩ እንደ አውሮፓውያን ቀመር ነው፡፡/


baba shenoudaየግብጽ ቤተ ክርስቲያን ወደ ሃያኛው መቶ ክፍለ ዘመን ሁለተኛ አጋማሽ ለመዝለቅ ያሳየችው ያልተጠበቀ መነቃቃት በዓለም የክርስትና እምነት ውስጥ ታላላቅ ከሚባሉት ታሪኮች መካከል አንዱ ነበር፡፡ በአብዛኛው የዓለም ክፍል ውስጥ ወንዶቹና ሴቶቹ የግብጽ ልጆች /ፈርዖኖች/Pharaohs/ በቤተ ክርስቲያናቸው አማካይነት የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመመሥረትና ወንጌልን ለማስፋፋት ያሳዩት ትጋት ተሰምቶ የማይታወቅ ነበር፡፡

ይህ መንፈሳዊ መንሠራራት ጅምሩን ያደረገው ግን ከግማሽ ምእተ ዓመት በፊት ሲሆን ይህም በአሥራ ዘጠኝ አርባዎቹና በአሥራ ዘጠኝ ሀምሳዎቹ በካይሮ፣ በጊዛና በአሲዩት በሚገኙ የቅብጥ/coptic/ የሰንበት ትምህርት ቤቶች እንቅስቃሴ ውስጥ ነበር፡፡ በሰንበት ትምህርት ቤቶች ውስጥ በሚደረጉ ትምህርታዊ ውድድሮች የተነሣሱት ወጣት ወንዶች ሕይወታቸውን ለእግዚአብሔር በመቀደስ፥ በበረሀ የሚኖሩ አባቶቻቸውን ለመከተል ወደዚያው ወጥተዋል፡፡ እነዚህ ወጣቶች በተለይም በሶርያውያን ገዳም ውስጥ በሚገኙት በአባ ቴዎፍሎስ /Bishop Theophilus/ ብቃት ያለው አመራር አማካይነት ለቤተ ክርስቲያናቸው የማነቃቃት ሥራ ለመሥራት ራሳቸውን አዘጋጁ፡፡

 

በ1959 ዓ.ም. አቡነ ቄርሎስ 6ኛ ፓትርያርክ ሆነው ከተሾሙ በኋላ የቀድሞዎቹ የሰንበት ትምህርት ቤት አገልጋዮች ከነበሩት መምህራን፣ መነኮሳትና ባሕታውያን መካከል ጥቂቶቹ ወደ መንበረ ፓትርያርክ ተጠርተው በቤተ ክርስቲያኒቱ ሕይወትና አደረጃጀት ውስጥ ቁልፍ የሓላፊነት ሥልጣን እንዲጨብጡ ተደረገ፡፡ ከእነዚህ ወጣቶች መካከል አቡነ እንጦንስ አል ሱሪያኒ /1954-2012//Fr. Antonyos (Anthony) El-Souryani/፣ በኋላም ሲኖዳ ተብለው የቅብጥ ቤተ ክርስቲያን የሥነ መለኮትና የትምህርት ተቋማት ጳጳስ /1962-71/ የተባሉትና በመጨረሻም አቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊ በሚል ስም የተሾሙት የአሁኑ ጳጳስና ፓትርያርክ የቀድሞው ናዚር ጋዪድ (Nazir Gayyid) ናቸው፡፡ የአቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊ የጵጵስና ሕይወት በታላቅ ጥረትና ጥልቀት ባለው መንፈሳዊነት የተቃኘ ስለ ነበር ሕይወቱን ለማጣት ተቃርቦ ለነበረው የስብከት ተቋም አዲስ ራእይና ሕይወት በመስጠት ስኬታማ ሊሆን ችሏል፡፡ ይህ በመሆኑም ከፍተኛ ወግ ተሰጥቶአቸው የነበሩትና ከተመሠረቱ ረዥም ጊዜያት ያስቆጠሩትን የቤተ ክርስቲያን ሥርዓቶችን ያዝ በማድረግ በአዲስ መንፈሳዊ ስሜት እንዲሞሉ አድርጓል፡፡

 

የአቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊ መንፈሳዊና ትምህርታዊ መነሻ አሁን ያለውን የቤተ ክርስቲያኒቷን የእንቅስቃሴ አቅጣጫ በስፋት የወሰነ ነው፡፡ ናዚር ጋዪድ /የአቡነ ሲኖዳ የመጀመሪያ የቤተሰብ ስማቸው ነው/ ሹብራ(Shubra) በሚገኘው የቅዱስ እንጦንስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሰንበት ትምህርት ቤት አባል የሆኑት ገና በ16 ዓመታቸው ነበር፡፡ በኋላ ግን የዚሁ ሰንበት ትምህርት አስተማሪ በመሆን በሺዎች የሚቆጠሩ ወጣት ግብጻውያንን በኢየሱስ ክርስቶስ እንዲያምኑ አድርገዋል፡፡

 

ናዚር ጋዪድ በብዙ መንገድ በላይ በቅብጥ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ለተቋቋመው አዲስ የወጣቶች አገልግሎት አጠቃላይ መሪ ሆነዋል፡፡ በ1947 ዓ.ም. በካይሮ ዩኒቨርሲቲ በእንግሊዝኛና በታሪክ የቢ.ኤ. (B.A.) ዲግሪያቸውን ተቀብለዋል፡፡ እስከ አሁን ድረስ ንግግራቸው፣ ስብከታቸውና መጻሕፍቶቻቸው እንከን የማይወጣላቸው የእንግሊኛ ቋንቋ ተጠቃሚ መሆናቸውን ያንጸባርቃሉ፡፡ በሥነ መለኮት ኮሌጅ ውስጥ የተሰጡትን ጥናቶች ብሩህ በሆነ የትምህርት ብቃት ስለ ፈጸሙ በዚያው ኮሌጅ ውስጥ የብሉይና የሐዲስ ኪዳን መምህር ሆነው ለመሾም በቅተዋል፡፡ ከዚህ በኋላ 1953 ዓ.ም. ሄልዋን (Helwan) በሚገኘው የምንኩስና ኮሌጅ ውስጥ የሙሉ ሰዓት አስተማሪ ሆነው ተመድበዋል፡፡

 

ሐምሌ 19 ቀን 1954 ዓ.ም. በሶሪያውያን ገዳም ውስጥ በሚገኙት በጳጳስ ቴዎፍሎስ (Bishop Tawfilus) አማካይነት ምንኩስናን ተቀብለዋል፡፡ በዚህ ዕለት ናዚር ጋዪድ የሚከተለውን ቃል ኪዳን ፈጽመዋል፡-

 

ምንኩስና ማለት ሀብትና ንብረትን፤ ዘመዶችንና ጓደኞችን፤ ሹመትንና ሥልጣንን አስመልክቶ ለዓለም ሙሉ ለሙሉ መሞት መሆኑን አረጋግጣለሁ፡፡ ምንኩስና የአምልኮና ራስን ለእግዚአብሔር የመስጠት ሕይወት መሆኑን አረጋግጣለሁ፡፡ የንስሓ፣ራስን የመተው፣ ፍጹም የመታዘዝ፣ የብቸኝነትና የድህነት ሕይወት መሆኑንም አረጋግጣለሁ፡፡ በእግዚአብሔር በመላእክቱና በቅዱስ መሠዊያው ፊት እንዲሁም ቅዱስ አባቴ በሆኑት በጳጳሱ ፊት፤ በተሰበሰቡ አባቶች ፊት፤ በመነኮሳት ፊት እና በዚህ ቅዱስ ጉባኤ ፊት ከዓለም ተለይቼ በድንግልና እና በንጽሕና እኖር ዘንድ ሕይወቴን ለእግዚአብሔር አቀርባለሁ፡፡ እውነተኛውን የምንኩስና ሥርዓት ለመቀበልና ቅዱሳን አባቶቻችን ለእኛ ያስቀመጡልንን ይህን መላእክታዊ የሕይወት ጠባይ ለመከተል ቃል እገባለሁ፡፡ ይህ ከሆነ ከአንድ ዓመት በኋላ ክህነትን ተቀብለዋል፡፡ ካህን፣ ጳጳስና ፓትርያርክ ሆነው በኖሩበት የሕይወት ዘመናቸው በሶሪያውያን ገዳም ውስጥ በምትገኘው የድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን የገቡትን ቃል ኪዳን እስከ አሁን ድረስ በታማኝነት ጠብቀዋል፡፡

 

በገዳሙ ውስጥ የቤተ መጻሕፍቱ ሓላፊ ሆኖ አገልግለዋል፡፡ እነዚህ ሥራዎች ጥናታቸውን በቤተ ክርስቲያን አባቶችና ሐኪሞች ላይ እንዲያደርጉ አስችለውታል፡፡ ይህ ይሁን እንጂ እርሳቸው ይናፍቁ የነበረው የብቸኝነትን ሕይወት ነበር፡፡ በመሆኑም በመጀመሪያ የመረጡት ከገዳሙ በሦስት ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚገኘውን ዋሻ ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ ይህንን የባሕታዊ መኖሪያ ከገዳሙ አሥር ኪ.ሜ. ርቀት ላይ በሚገኘው ባኸር አል ፋራይ (Bahr al-Farigh) ዋሻ እንዲለውጡ ሆነዋል፡፡ በ1984 ዓ.ም. መግቢያ ላይ “ባሕታዊው” በሚል ርዕስ የጻፉት ግጥም በ1954 ዓ.ም. በሰንበት ትምህርት ቤቱ መጽሔት ላይ ታትሞ ወቷል፡፡

 

ከመጽሔቱ የተወሰደ፡-

ብቻዬን በበረሀ ውስጥ የራሴን ነገር እየሰላሰልሁ፤

በተራራው ጫፍ  ባለ ዋሻ ገብቼ ተከልያለሁ፤

እና አንድ ቀን ትቼው እሔዳለሁ፤

የምኖርበትን ወደማላውቀው፡፡


በ1959 ዓ.ም. ፓትርያርኩ ቄርሎስ 6ኛ የግል ጸሐፊያቸው አድርገው ቢሾሟቸውም አባ እንጦንዮስ የመረጡት የብቸኝነት ሕይወት ነበር፡፡ አባ እንጦንስ ለብዙ ዓመታት የጵጵስና ማዕረግ እንዲቀበሉ የተለያዩ ጫናዎች ቢደረጉባቸውም ሁሉንም በተሳካ ሁኔታ ሊከላከሉ ችለዋል፡፡ ይሁን እንጂ በመስከረም ወር 1962 ዓ.ም. ፓትርያርኩ አቡነ ቄርሎስ በገዳሙ ውስጥ አለመግባባት ስለ ፈጠሩት ጥቂት የአስተዳደር ነክ ጉዳዮች ከባሕታዊው ከአባ እንጦንስ ጋር ለመወያየት በሚል ካይሮ ወደሚገኘው መንበረ ፓትርያርክ እንዲመጡ ያስጠሯቸዋል፡፡ አባ እንጦንስ በፓትርያርኩ ፊት ተንበርክከው ይቅርታ በመጠየቅና ከአስተዳደር ሥራ እንዲለዩ በማሳሰብ ለጥያቄያቸው መልስ በመጠባበቅ ላይ ሳሉ ፓትርያርኩ ቄርሎስ እጆቻቸውን በባሕታዊው ራስ ላይ በመጫን የቅብጥ ቤተ ክርስቲያን የሥነ መለኮት እና የትምህርት ተቋማት ጳጳስ አድርገው ይሾሟቸዋል፡፡

 

ይህ ሹመት በመንበረ ፓትርያርኩ መስከረም 30 ቀን 1962 ዓ.ም. ተሰጠ፡፡ ከዚህ በኋላ እኔ ራሴ /የዚህ ጽሑፍ ጸሐፊ/ “እንኳን ደስ አልዎ” በማለት ለአቡነ ሲኖዳ ለጻፍኩላቸው ደብዳቤ የጻፉልኝ የመልስ ደብዳቤ ከዚህ የሚከተለው ነው፡-

 

“ከአምላካችንና ከመድኀኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ የሆነ ጸጋና ሰላም ለአንተ ይሁን፡፡ ወደ እኔ ስለላክሃቸው የ”እንኳን ደስ አልዎ” መልካም ቃላት አመሰግንሃለሁ፡፡ ወዳጅነትህንና ፍቅርህን በጭራሽ ልዘነጋ አልችልም፡፡ እውነቱን ለመናገር ግን አሁን ለገጠመኝ ሁኔታ የሚገባኝ የማጽናኛ ደብዳቤ እንጂ የእንኳን ደስ ያለህ ደብዳቤ አልነበረም፡፡ አንድ መነኩሴ የበረሀውን ፀጥታ ትቶ በከተማ ሁከት ለመታጀብ በመሔዱ እንዴት እንኳን ደስ ያለህ ሊባል ይችላል? ማርያም ከክርስቶስ እግር አጠገብ ያለ ቦታዋን ትታ ከማርታ ጋር በኩሽና ለመገኘት በመሔዷ እንኳን ደስ አለሽ የሚላት ማነው? በእርግጥም ይህ ለእኔ በጣም የሚያሳፍር ነገር ነው፡፡ ለጵጵስና የተመረጥሁባትን ያቺን ቀን የማስታውሳት በዕንባና በሰቆቃ ነው፡፡ እውነቱን ለመናገር ግን የብቸኝነትና የተመስጦ ክብር ከመናገር በላይ ነው፡፡ ከኤጲስ ቆጶስነትና ከጳጳስነት ጋር አይነጻጸርም፡፡ ውድ ወዳጄ ሆይ፤ እውነተኛው መቀደስ ልብን ለእግዚአብሔር ቅዱስ ቤተ መቅደስ አድርጎ መቀደስ ነው፤ እርሱ በመጨረሻው ቀን የሚጠይቀን የእረኝነት ማዕረጋችንን ሳይሆን የልባችንን ንጽሕና ነውና፡፡ ይህን ደብዳቤ የጻፍሁልህ ከምወደውና ዋዲ አል-ንጥራን (Wadi al-Natrun) ውስጥ ከሚገኘው ከባሕር አል ፋራይ (Bahr al-Farigh) ዋሻ ሆኜ ነው፡፡ ወደ ካይሮ ከመመለሴ በፊት የምቆየውና የጥምቀትን በዓል የማከብረው በዚህ ዋሻ ውስጥ ነው፡፡››

 

ይሁን እንጂ በተገኘው አመቺ ጊዜ ሁሉ ጳጳሱ አባ ሲኖዳ የሚሔዱት ወደዚህ ገዳም ነው፡፡ በክርስቲያን የትምህርት መስክ ውስጥ የአቡነ ሲኖዳ አመራር ዋጋውን ያገኘው በ1969 ዓ.ም. የመካከለኛው ምሥራቅ የሥነ መለኮት ኮሌጆች ኅብረት ፕሬዝዳንት (President of the Association of Middle East Theological Colleges) ሆነው ሲመረጡ ነው፡፡ የአቡነ ሲኖዳ እጅግ ጠቃሚ የአገልግሎት ዘርፍ በየሳምንቱ የሚያቀርቧቸው ስብከቶች አቀራረብ ሲሆን በዚህም ለሥነ መለኮታዊና ለማኅበረሰባዊ ጥያቄዎች መልስ ሰጥተዋል፡፡ በሺዎች የሚቆጠሩ ወጣቶችም የዚህ አገልግሎት ተሳታፊዎች ሆነዋል፡፡ አቡነ ሲኖዳ የሳምንቱን እኩሌታ በካይሮና በእስክንድርያ በማስተማርና በመስበክ ከቆዩ በኋላ የሳምንቱን እኩሌታ የሚያሳልፉት በዚህ ገዳም ውስጥ ነው፡፡

 

በእነዚህ ዓመታት ውስጥ ከቅብጥ ቤተ ክርስቲያን ዓላማዎች አንዱ ለመቶ ዓመታት አብሯት ከቆየው የሥነ መለኮት ልዩነት ራስዋን ነጻ ማውጣት ነበር፡፡ አቡነ ሲኖዳ ቤተ ክርስቲያናቸውን በመወከል ብዛት ባላቸው የአብያተ ክርስቲያናት ኅብረት ጉባኤዎች ላይ ተሳትፈዋል፡፡ የትምህርት ጳጳስ ሳሉ ለመጨረሻ ጊዜ የተሳተፉበት ጉባኤ በ1971 ዓ.ም. ቪየና ውስጥ በምሥራቃውያን ኦርቶዶክስና በካቶሊካውያን አብያተ ክርስቲያናት መካከል የተደረገው የመጀመሪያው ጠቃሚ የምክክር ጉባኤ ነው፡፡ ይህ የሆነው የእስክንድርያ ፓትርያርክ ሆነው ሊሾሙ ልክ አንድ ወር ሲቀራቸው ነበር፡፡ በዚህ ጉባኤ ላይ አቡነ ሲኖዳ የእስክንድርያው ቅዱስ ቄርሎስ ያዘጋጀውን የክርስቶስ ትምህርት ተቀባይነት እንዲያገኝ አድርገዋል፡፡ ይህ አንቀጽ ኋላ ላይ በሮማው ጳጳስ በዮሐንስ ጳውሎስ አራተኛና በአቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊ በይፋ ተቀባይነትን አግኝቷል፡፡

 

ተቀባይነት ያገኘውና የእስክንድርያው ቅዱስ ቄርሎስ ስለ ክርስቶስ ያስተማረው ትምህርት አንቀጽ የሚከተለው ነው፡-

“እኛ ሁላችን አምላካችን እግዚአብሔር መሆኑንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋ የለበሰው ቃል መሆኑን እናምናለን፡፡ እርሱ በመለኮቱና ሰው በመሆኑ ፍጹም እንደሆነ እናምናለን፡፡ አምላክነቱ ከሰውነቱ ለቅጽበት እንኳ እንዳልተለየም እናምናለን፡፡ ሰው መሆኑ ከመለኮቱ ጋር ያለ መቀላቀለ፣ ያለ መለወጥ፣ ያለ መከፋፈልና ያለ መለያየት የሆነ ነው፡፡”


ፓትርያርኩ አቡነ ቄርሎስ አራተኛ መጋቢት 9 ቀን 1971 ዓ.ም. በሞተ ሥጋ ሲለዩ ቅዱስ ሲኖዶሱ ማርች 22 ቀን 1971 ዓ.ም. ተከታዩን ፓትርያርክ ለመምረጥ ዝግጅት ማድረግ እንዳለበት ወሰነ፡፡ ጥቅምት 29 ቀን 1971 ዓ.ም. ይፋ የነበረው ምርጫ ከአምስት ወደ ሦስት እጩዎች ዝቅ አለ፡፡ ከዚህ በኋላ አይማን ሙኒር ካሚል የተባለና ዐይኖቹ በጨርቅ የታሰሩ አንድ ልጅ የዕጩዎቹ ጳጳሳት ስሞች ተጽፈውባቸው ከተጠቀለሉት ቁርጥራጭ ወረቀቶች መካከል አንዱን በማንሣት ለከተማዋ ጳጳስ ለእንጦኒዮስ ሰጠ፡፡ እርሳቸውም ለቅብጥ ቤተ ክርስቲያን እረኛ ይሆን ዘንድ የተመረጠው ጳጳሱ ሲኖዳ መሆኑን በይፋ አስታወቁ፡፡ ከሁለት ሳምንታት በኋላ ኅዳር 14 ቀን 1971 ዓ.ም. ጳጳሱ ሲኖዳ “ቅዱስነታቸው አቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊ በማርቆስ መንበር 117ኛው ፓትርያርክ” ተብለው በይፋ ተሰየሙ፡፡

 

ምንም እንኳን ጳጳስና ፓትርያርክ ቢሆኑም በሥነ መለኮት ኮሌጅና በቅብጥ ጥናት ከፍተኛ ተቋም ውስጥ ማስተማራቸውን አላቋረጡም፡፡ በመሆኑም በታሕታይ ግብጽና በላዕላይ ግብጽ ውስጥ ቅርንጫፍ የሆኑ ስድስት ተጨማሪ የሥነ መለኮት ኮሌጆች ሲከፈቱ ሌሎች ተጨማሪ ሦስት ኮሌጆች በዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካና በአውስትራሊያ ተመሠረቱ፡፡

 

እንደ ሊቅነታቸው አቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊ በቅብጥ ላይ የሚደረጉ የተለያዩ ጥናቶችን አበረታተዋል፤ በዚህም ታላቁ የቅብጥ ኢንሳይክሎፒዲያ እንዲታተም አድርገዋል፡፡ በሚያዝያ ወር 1988 ዓ.ም. በመንበረ ፓትርያርኩ ውስጥ ያለው የቅብጥ መዝገብ ቤት በማይክሮ ፊልም እንዲነሣ አል አህራም (Al-Ahram) ከተባለ የዜና ድርጅት ጋር ኮንትራት ተፈራርመዋል፡፡

 

የቤተ ክርስቲያኗ የበላይ ጠባቂ በመሆናቸው ከ80 የሚበልጡ ጳጳሳትንና ከ500 የሚበልጡ ካህናትን ግብጽ ውስጥ ለምትገኘው ለቅብጥ ቤተ ክርስቲያንና በውጪ ለሚኖሩ የቅብጥ አብያተ ክርስቲያናት አማኞች ሾመዋል፡፡ በየጊዜው ከካህናቱ አባላት ጋር የሚያደርጓቸው ሴሚናሮች የካህናቱንና የጳጳሳቱን የእረኝነቱን፣ የመንፈሳዊነቱንና የትምህርቱን ሕይወት አበረታትዋል፡፡ እርሳቸው ለወጣቱ ትውልድ ልዩ ትኩረት ስለሰጡ በአቡነ ሙሳ የበላይ ሓላፊነት በጣም ድንቅ የሆነ የወጣቶች የአገልግሎት ዘርፍ እንዲቋቋም አድርገዋል፡፡ ታይቶ የማይታወቅ የአብያተ ክርስቲያናት ቁጥር በተለይም በውጪ ሀገራት እየጨመረ ስለመጣ አቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊ መጠኑ የበዛ ቅዱስ ሜሮን ወይም የምሥጢር ዘይት በ1981፣ በ1983፣ በ1993 እና በ1995 ዓ.ም. በቅዱስ ቢሶይ ገዳም ውስጥ ባርከዋል፡፡ የክርስቲያኖች አንድነት እንዲኖር ጥልቅ ፍላጎት ስለነበራቸው የተሻለ የምክክር መግባባት ይፈጠር ዘንድ ሰፊ ጊዜና ጥረት አድርገዋል፡፡ በክርስቲያኖች አንድነት ላይ ምንጊዜም አጽንዖት ሰጥተው የሚናገሩት የክርስቲያኖች አንድነት ሊመሠረት የሚገባው በእምነት ላይ እንጂ በሥልጣን ላይ አለመሆኑን ነው፡፡ እስከ ዛሬ ድረስ በምሥራቅ ኦርቶዶክስ፣ በሮማ ካቶሊክ፣ በአንጀሊካን፣ በፕሬስባይቴሪያን፣ በስዊድን ሉተራን እና በተሐድሶ አብያተ ክርስቲያናት መካከል የሥነ መለኮት ውይይት እንዲደረግ አነሣሥተዋል፡፡

 

ይህ በመሆኑም በግንቦት ወር 1973 ዓ.ም. አቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊ በሮማው ጳጳስ በጳውሎስ 6ኛ ጥሪ ሮምን እንዲጎበኙ ተጋብዘው ነበር፡፡ ከ451 ዓ.ም. በኋላ በአንድ እስክንድርያዊና በአንድ ሮማዊ ጳጳስ መካከል እንዲህ ያለው ግንኙነት ሲደረግ ይህ የመጀመሪያው ነው፡፡ በዚህ ግንኙነት ሁለቱም በክርስቶስ ላይ ያላቸውን የጋራ እምነት በፊርማቸው አጽድቀዋል፡፡ በ1979፣ በ1987 እና በ1995 ዓ.ም. አቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊ ከካንተርበሪ ሊቀ ጳጳስ (Archbishop of Canterbury) ጋር ተገናኝተው በቅዱሳት መጻሕፍት ላይ ያላቸውን የጋራ ግንዛቤ ተወያይተዋል፡፡ በኖቬምበር ወር 1988 ዓ.ም. ደግሞ በቅብጥና በፕሬስባይቴሪያን አብያተ ክርስቲያናት መካከል የሥነ መለኮት ክርክር እንዲካሔድ አበረታተዋል፡፡ ይህ ክርክር በመካከለኛው ምሥራቅ በሚገኙ ኦርቶዶክሶችና ፕሮቴስታንቶች መካከል ተፈጥረው የነበሩትን አንዳንድ የሥነ መለኮት የአመለካከት ችግሮት ለማስታረቅ መንገዱን ጠርጓል፡፡

 

ከሌሎች የኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት ጋር ያለውን ግንኙነት በተመለከተ አቡነ ሲኖዳ ሳልሳዊ በደማስቆ፣ በኢስታንቡል፣ በሞስኮ፣ በቡካሬስትና በሶፊያ ያሉትን የኦርቶዶክስ መንበረ ፓትርያርኮች ጎብኝተዋል፡፡ በመካከለኛው ምሥራቅ ታላቅ በአፍሪካም ጥንታዊት የሆነችው ቤተ ክርስቲያን መሪ እንደመሆናቸው መጠን ቤተ ክርስቲያናቸው በመካከለኛው ምሥራቅ የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት እና ከመላው አፍሪቃ አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ጋር ላላት ተሳትፎ ልዩ ትኩረት ሰጥተዋል፡፡

 

በየካቲት ወር 1991 ዓ.ም. በካንቤራ አውስትራሊያ በተካሔደው በ7ኛው የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ጉባኤ ላይ ለመገኘት አሥራ አንድ የቅብጥ አባላትን ያካተተውን የልዑካን ቡድን መርተዋል፡፡ በስብሰባው ማብቂያ ላይ ከዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ፕሬዘዳንቶች መካከል አንዲ ሆነው ተመርጠዋል፡፡ በኅዳር ወር 1994 ዓ.ም. ቆጵሮስ (Cyprus) ውስጥ በተካሔደው ስብሰባ ላይ ደግሞ የመካከለኛው ምሥራቅ አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት አራት ፕሬዘዳንቶች መካከል አንዱ ሆነው ተመርጠዋል፡፡ ምንም እንኳ የዓለም የክርስትና እምነትን ለማገልገል ሰፊ ጊዜያቸውን መሥዋዕት አድርገው ቢያቀርቡም ሲኖዳ ሳልሳዊ በልባቸው መነኩሴ መሆናቸው አልቀረም ነበር፡፡

 

ከዚህ ሌላ በመካከለኛው መቶ ክፍለ ዘመን ከሰው የተራቆቱ ብዛት ያላቸው ገዳማት እንዲታደሱና ተመልሰው እንዲገነቡ መሣሪያ ሆነው ቆይተዋል፡፡ የጵጵስና መኖሪያቸው የተመሠረተው ቅዱስ ቢሶይ ገዳም ውስጥ ነው፡፡ ይህ መኖሪያቸው በውስጡ የጸሎት ቤት፣ የስብሰባና የስብከት አዳራሾችን እና እንግዳ መቀበያ ክፍሎች ያካተተ ነው፡፡ አቡነ ሲኖዳ ሳልሳዊ የእያንዳንዱን ሳምንት እኩሌታ በተመስጦና በአርምሞ የሚያሳልፉት በዚህ ገዳም ውስጥ ነው፡፡

 

በ1971 ዓ.ም. ከግብጽ ውጪ ለሚኖሩ ግብጻውያን የነበሩት የቅብጥ አብያተ ክርስቲያናት ሰባት ብቻ ነበሩ፡፡ ዛሬ ግን በዩናይትድ ስቴትስና በካናዳ ብቻ አንድ መቶ፣ በአውስትራሊያ ሃያ ስድስት በአውሮፓ ደግሞ ከሠላሳ የሚበልጡ አብያተ ክርስቲያናት አሉ፡፡ በውጪ ሀገራት በሚገኙ በእነዚህ አብያተ ክርስቲያናት ውስጥ የሚያገለግሉ አሥራ አምስት የቅብጥ ጳጳሳትም አሉ፡፡

 

በ1994 ዓ.ም. በእንግሊዝ ደሴቶች (British Isles) ላይ የሚኖሩና አሥራ ዘጠኝ የሚደርሱ የእንግሊዝ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ሀገረ ስብከቶች ከቅብጥ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ጋር ሙሉ ኅብረት ፈጥረዋል፡፡ በ1994 ዓ.ም. በተከበረው የበዓለ አምሳ ላይ አባ ሱሪፌል የግላስተንበሪ (Glastonbury) ጳጳስ ሆነው ተሾመዋል፡፡ ኤርትራ የራስዋን መንግሥት ካቋቋመችና አቶ ኢሳይያስ አፈወርቂ የኤርትራ ፕሬዝዳንት ሆነው ከተመረጡ በኋላ በመንበረ ማርቆስ የስብከት አሰጣጥ ደንብ የሚመራ ነጻ የኤርትራ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን እንዲቋቋምላቸው አቡነ ሲኖዳ ሳልሳዊን ጠይቀዋል፡፡ ከዚህ በኋላ የቅብጥ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ቅዲስ ሲኖዶስ መስከረም 28 ቀን 1993 ዓ.ም. ባካሔደው ስብሰባ የኤርትራውያን ክርስቲያኖችን ጥያቄ ለመቀበል ተስማምቷል፡፡ በዚህ መሠረት 1994 ዓ.ም. በዋለው በዓለ ሀምሳ አቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊ አምስት ኤርትራውያን ጳጳሳትን በመሾም የኤርትራውያንን የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ነጻ ሲኖዶስ ለመመሥረት መሠረት አስቀመጡ፡፡ ግንቦት 7 ቀን 1998 ዓ.ም. ቅዱስነታቸው አቡነ ሲኖዳ የ93 ዓመቱን ጳጳስ አቡነ ፊልጶስን የኤርትራ የመጀመሪያው ፓትርያርክ በማድረግ ሾሙ፡፡ ካይሮ በሚገኘው የቅዱስ ማርቆስ ካቴድራል ውስጥ በዓለ ሲመቱ ሲከናወን ከሀምሳ የሚበልጡ የቅብጥ ጳጳሳትና ሰባት የኤርትራ ጳጳሳት ተገኝተው ነበር፡፡

 

አስቀድመን ካነሳነው ተጋድሎአቸው መካከል፥ ፕሬዝዳንት አንዋር አል ሳዳት አቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊን በትክክል ባለመረዳት በተደጋጋሚ ከሰዋቸው እንደነበር ነው፡፡ በተለይም አቡነ ሲኖዳ ግንቦት 14 ቀን 1980 ዓ.ም. በፓርላማው ፊት ያሰሙት ንግግር በቅብጥ ቤተ ክርስቲያንና በግብጽ መንግሥት መካከል ያለውን የፖለቲካ አየር ክፉኛ በከለው ተባለ፡፡ ይህ አሳዛኝ ሁኔታ ተደማምሮ መስከረም 3 ቀን 1981 ዓ.ም. ፕሬዝዳንት ሳዳት ከቤተ መንግሥት ባስተላለፉት ትእዛዝ መሠረት አቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊ በቅዱስ ቢሾይ ገዳም በግዞት እንዲቀመጡ አደረጉ፡፡ ከዚህ በተመሳሳይ ጊዜ ስምንት ጳጳሳት፣ ሃያ አራት ቀሳውስትና ሌሎች እውቅና ያላቸው ብዙ የቅብጥ ቤተ ክርስቲያን አባላት ታሠሩ፡፡ ሳዳት ይህን ካደረጉ በኋላ አምስት ጳጳሳትን ያቀፈ አንድ የቅብጥ ቤተ ክርስቲያን የአስተዳደር ኮሚቴ አዘጋጁ፡፡ ቅዱስ ሲኖዶሱ ግን የቅብጥ ቤተ ክርስቲያን መሪ አቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊ መሆናቸውን በአጽንዖት አረጋገጠ፡፡ ይህ ሁሉ ሲሆን ፕሬዝዳንት ሳዳት አቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊን ይጠሩ የነበረው “የቀድሞው ፓትርያርክ” እያሉ ነበር፡፡

 

አቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊ በቅዱስ ቢሶይ ገዳም በግዞት ሳሉ ዓለም አቀፉ የሰብአዊ መብት ተሟጋች አምነስቲ ኢንተርናሽናል (Amnesty International) “የኅሊና እስረኛ” (‘Prisoner of Conscience’) በማለት ነሐሴ 26 ቀን 1983 ዓ.ም. በይፋ ሰይሟቸዋል፡፡ በዓለም ዙሪያ የሚኖሩ ብዛት ያላቸው ክርስቲያኖች ጥልቅ ሃዘናቸውን ገልጠዋል፡፡ ይፈቱ ዘንድ በሰኔ ወር 1982 ዓ.ም. እና በኅዳር ወር 1984 ዓ.ም. ልዩ የጸሎት መርሐ ግብር ተደርጎላቸዋል፡፡ የጊዛው ጳጳስ ዱማዴዎስ የቀድሞ ባልንጀራቸውን በየሳምንቱ ይጠይቋቸው ነበር፡፡ ፕሬዝዳንት ሳዳት ነሐሴ 3 ቀን 1981 ዓ.ም. ያስተላለፉትን የግዞት ትእዛዝ ፕሬዝዳንት ሙባረክ ታኅሣሥ 2 ቀን 1985 ዓ.ም. ሻሩት፡፡ አቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊ ከስደት ዓመት ከአራት ወራት ግዞት በኋላ ታኅሣሥ 4 ቀን 1985 ዓ.ም. በአሥራ አራት ጳጳሳት ታጅበው ወጡ፡፡ በሚቀጥለው ቀን የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን የልደት በዓል በቅዱስ ማርቆስ ካቴድራል ሲያከብሩ ከአሥር ሺህ የሚበልጥ ሕዝብ ተገኝቶ ፓትርያርኩን ተቀብሏል፡፡

 

ከዚህ በኋላ በመንግሥትና በቤተ ክርስቲያን መካከል ያለው ግንኙነት አመርቂ በሆነ መልኩ ተሻሻለ፡፡ ከብዙኀኑ የእስልምና እምነት ተከታዮች ጋር ስለ ተፈጠረው መልካም ግንኙነት ምስክር የሚሆነው በረመዳን የጾም ወር ውስጥ ቅዱስነታቸው አቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊ በፖለቲካውና በሃይማኖቱ ውስጥ የሚገኙትን የሀገሪቱን የበላይ አመራር አባላት በየዓመቱ የአፍጥር መጋበዛቸው ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ከ1986 ዓ.ም. ጀምሮ የአል አዛር ሼህ፤ ታላቁ ሙፍቲ እና የውጪ ጉዳይ ሚኒስትሩ ከሌሎች ሰዎች ጋር በመሆን ትርጉም ባለው የመልካም ፈቃድ ሰላማዊ ሰልፍ ላይ እየተሳተፉ ነው፡፡ ይህ ይሁን እንጂ አቡነ ሺኖዳ ሣልሳዊ የአናሳ ክርስቲያኖች መሪ ተብለው ሊጠሩ እንደማይፈቅዱ በተደጋጋሚ ገልጸዋል፡፡ በመሆኑም “ቅብጥ እንደ መሆናችን በግብጽ ክፍል የምንኖር ግብጻውያን ነን፡፡” በማለት አዘውትረው ይናገራሉ፡፡

 

ምንጭ፡-

  • ST.JOHN-NOVEMBER 2004
  • አዘጋጅ፡- ኦክተር አቶ ሜናርደስ
  • ተርጓሜ፡- አያሌው ዘኢየሱስ

የዐብይ ጾም ስብከት /ክፍል 6/

መጋቢት 20/2004 ዓ.ም.

በአያሌው ዘኢየሱስ

 

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

 

በዐቢይ ጾም ስድስተኛ ሳምንት ውስጥ የምናነበው ወንጌል የሚያሳስበን ስለ በጎና ታማኝ አገልጋይ የተነገረውን ምሳሌ ነው፡፡ በዚህ የወንጌል ንባብ ውስጥ ጌታ በምሳሌ አድርጎ በመጨረሻው የፍርድ ቀን ሰዎች እንደ ሥራቸው እንደሚዳኙ በሰፊው አስተምሯል፡፡ በዚህ ምሳሌ ውስጥ አንድ ጌታ ለሦስት ባሮቹ ለእያንዳንዳቸው እንደ አቅማቸው ለአንዱ አምስት መክሊት፣ ለአንዱ ሁለት መክሊትና ለሌላው ደግሞ አንድ መክሊት ከሰጣቸው በኋላ ነግዱና አትርፉ በማለት እርሱ ወደ ሌላ አገር መሄዱ ተገልጦአል፡፡ በዚህም መሠረት አምስት መክሊት የተቀበለው የመጀመሪያው ባሪያ በተሰጠው አምስት መክሊት ቆላ ወርዶ ደጋ ወጥቶ ከነገደ በኋላ አምስት ተጨማሪ መክሊቶችን በማትረፍ አኖረ፡፡ ሁለት መክሊቶችን የተቀበለው ሁለተኛው ባሪያም በተሰጡት አምስት መክሊቶች ከነገደ በኋላ ሌሎች ተጨማሪ ሁለት መክሊቶችን አትርፎ አስቀመጠ፡፡ ሦስተኛው ባሪያ ግን ከእነዚህ ሁለት ባሪያዎች በተለየ ሳይወጣና ሳይወርድ፣ ሳይደክምና ሳያተርፍ በአቅሙ መጠን በተሰጠው አንድ መክሊት ሥራ ሳይሠራ እንዲሁ ወስዶ ጉድጓድ በመቆፈር ቀበረው፡፡

ይህ ሁሉ ከሆነ በኋላ ለእነዚህ ሦስት ባሪያዎች በመጠን የተለያዩ መክሊቶችን ሰጥቶ ወደ ሩቅ አገር ሄዶ የነበረው ጌታቸው ወደ እነርሱ ተመልሶ መጣ፡፡ ከዚያም እያንዳንዳቸው በየተራ ወደ እርሱ እያስገባ በተሰጧቸው መከሊቶች ምን እንደሠሩ ይጠይቃቸውም ይቆጣጠራቸውም ጀመር፡፡ በዚህ መሠረት አምስት መክሊቶችን የተቀበለው የመጀመሪያው ባሪያ በጌታው ፊት ቀርቦ በተሰጡት አምስት መክሊቶች ሌሎች ተጨማሪ መክሊቶችን በማትረፍ በድምሩ አሥር መክሊቶችን ለጌታው አስረከበ፡፡ ሁለተኛውም እንዲሁ በተሰጡት ሁለት መክሊቶች ሌሎች ሁለት መክሊቶችን አትርፎ አሁን በእጁ ላይ ያሉትን አራት መክሊቶች ለጌታው አስረከበ፡፡ በዚህ ጊዜ የእነዚህ ሁለት ባሪያዎች ጌታ በእነርሱ ደስ በመሰኘት ለሁለቱም አንተ መልካም፣ በጎና ታማኝ ባሪያ በጥቂቱ ታምነሃልና በብዙ ስለምሾምህ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ በማለት ወደ መንግሥቱ አስገባቸው፡፡

ምንም ሥራ ሳይሠራና ሳያተርፍ የተሰጠውን አንድ መክሊት ጉድጓድ ውስጥ የቀበረው ሦስተኛው ባሪያ ግን ባዶ እጁን መቅረቡ ሳያንሰው በድፍረት ጌታ ሆይ፡- ካልዘራህበት የምታጭድ፤ ካልበተንህበት የምትሰበስብ ጨካኝ ሰው መሆንህን ስለማውቅና ስለ ፈራሁ መክሊትህን ጉድጓድ ቆፍሬ በመቅበር አቆይቼልሃለሁና እነሆ ተረከበኝ የሚል መልስ ሰጠ፡፡ በዚህ ጊዜ ንጉሡ እጅግ ስለ ተቆጣ አንተ ክፉና ሃኬተኛ ባሪያ፤በእርግጥ እንዲህ ዓይነት ሰው መሆኔን ታውቃለህን? ካወቅህ ደግሞ ገንዘቤን ለሚነግዱበት ወይም ለሚለውጡ ሰዎች በመስጠት እነርሱ እንዲያተርፉበት ማድረግና እኔ ተመልሼ ስመጣ ከነትርፉ ከእነርሱ መቀበል እንድችል ማድረግ ትችል ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ይህን ሳታደርግ ጭራሹኑ በድፍረት እነዚህን በእውነት ላይ ያልተመሠረቱ ክፉ ቃላትን ስለ ተናገርህ ቅጣት ይገባሃል በማለት ለወታደሮቹ፡- ያለውን መክሊት ውሰዱና አሥር መክሊት ላተረፈው ጨምሩለት፤ ላለው ይሰጠዋል ይበዛለትማል፤ ከሌለው ግን ያው ያለው እንኳ ይወሰድበታል፡፡ ስለዚህ የማይጠቅመውን ባሪያ ወደ ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ወዳለበት ወደ ውጪ አውጡት በማለት አዘዛቸው፡፡

ጌታችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ምድር ላይ ሳለ ለሕዝቡና ለደቀ መዛሙርቱ ትምህርቱን ቃል በቃል ወይም በሰምና ወርቅ ወይም በምሳሌ አስተምሮአቸዋል፡፡ በዚህ መሠረት እርሱ ይህን ትምህርት ያስተማረው በምሳሌ ነው፡፡ ጌታ ትምህርቱን በምሳሌ ያስተምር የነበረው አስቀድሞ በነቢዩ ዳዊት «አፌን በምሳሌ እከፍታለሁ፤ ከቀድሞ ጀምሮ ያለውንም ተምሳሊት እናገራለሁ፡፡» (መዝ 77፥2) ተብሎ የተነገረውን የትንቢት ቃል ለመፈጸምና ቃሉን የሚሰሙት ተማሪዎቹ የሚማሩት ትምህርት ሳይገባቸው እየተጠራጠሩ ወደ ቤታቸው እንዳይመለሱ ለማድረግ ነበር፡፡ በመሆኑም ኢየሱስ ክርስቶስ በማቴዎስ ወንጌል ውስጥ ብቻ ከሰባት በማያንሱ ምሳሌዎች ስለምትመጣው መንግሥቱ በስፋት አስተምሯል፡፡ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ የወንጌልን ቃል በዚህ ዓለም ላይ ሲዘራ ዘሩ በተለያዩ የሙያ ዘርፎች ላይ በተሠማሩ ሰዎች ልብ ውስጥ በተለያዩ ምሳሌዎች አማካኝነት ይዘራ ነበር፡፡ ይህ በመሆኑም ጌታ ቃሉን ለገበሬዎች በዘርና በእንክርዳድ እንዲሁም በሰናፍጭ ቅንጣት፣ ለእናቶች በእርሾ፣ ለነጋዴዎች በመዝገብና በዕንቁ፣ ለዓሣ አጥማጆች በመረብ. . . ወዘተ እየመሰለ በምሳሌ ያስተምራቸው ነበር፡፡ ከእነዚህ በተጨማሪ በአሥሩ ቆነጃጅት፣ በሰርግ ቤት፣ በበግና በፍየል. . . ወዘተ በተመሳሳይ ሁኔታ ስለ መንግሥቱ በስፋት በምሳሌ አስተምሯል፡፡ ጌታ ይሁን ያደርግ የነበረው ትምህርቱ ለተማሪዎቹ እንዲብራራላቸውና ግልጽ እንዲሆንላቸው ነበር፡፡

በዐቢይ ጾም ስድስተኛ ሳምንት ሰንበት ውስጥ የምናነበው ንባብ፣ የምንሰበከው ስብከትና የምንዘምረው መዝሙር የሚነግረንም ስለ አንድ በጎናና ታማኝ ባሪያ በምሳሌ የተነገረውን ትምህርት ነው፡፡ ስለዚህ በዚህ የወንጌል ቃል መሠረት «ወደ ሌላ አገር የሚሄድ ሰው» ተብሎ የተጠቀሰው ሰው በዳግም ምጽአቱ ወደዚህ ምድር ተመልሶ ከመምጣቱ በፊት ወደ ቀደመ ክብሩ የተመለሰውን ቅን ፈራጅ አምላካችን በሆነው በኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ በምሳሌው ውስጥ የተጠቀሱት ባሪያዎች የሚወክሉት ምዕመናንን ወይም እኛን ነው፡፡ መክሊት የተባለው በጎ የሚያሰኘው በጎና መልካም ሥራ ነው፡፡ የመጀመሪያዎቹ ሁለት ባሪያዎች ወይም አገልጋዮች የሚመሰሉት ሥራን ከሃይማኖት ጋር አስተባብረው የያዙትን ጻድቃን ሲሆን መክሊቱን ጉድጓድ በመቆፈር የቀበረው ክፉና ሃኬተኛ ባሪያ ደግሞ ምግባርና ሃይማኖት የሌላቸው የኃጢአተኛ ሰዎች ምሳሌ ነው፡፡

በዚህ መሠረት ጌታችንና አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአጭር ቁመትና በጠባብ ደረት በመካከላችን ተገኝቶ ስለ መንግሥተ የምትናገረውን ወንጌል ከሰበከልን በኋላ ለእያንዳንዳችን አንድ፣ ሁለትና አምስት መክሊቶችን በመስጠት ለፍርድ እስከምመጣ ደረስ ነግዳችሁና አትርፋችሁ ጠብቁኝ ብሎን በዕርገቱ ወደ ቀደመ ክብሩ ተመልሶ  ሄዷል፡፡ በመሆኑም ሁላችንም ከእግዚአብሔር የተለያዩ መክሊቶችን ተቀብለናል፤ እንድንነግድባቸውና እንድናተርፍባቸው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ይህን አስመልክቶ ሲናገር እንዲህ ብሏል፡- «ለአንዱ ጥበብን መነገር በመንፈስ ይሰጠዋልና፤ለአንዱም በዚያው መንፈስ እውቀትን መናገር ይሰጠዋል፤ለአንዱም በዚያው መንፈስ እምነት፤ለአንዱም በአንዱ መንፈስ የመፈወስ ስጦታ፤ለአንዱም ትንቢትን መናገር፤ለአንዱም መናፍስትን መለየት፤ለአንዱም በልዩ ዓይነት ልሳን መናገር፤ለአንዱም በልሳኖች የተነገረውን መተርጎም ይሰጠዋል፤ይህን ሁሉ ግን ያ አንዱ መንፈስ እንደሚፈቅድ ለእያንዳንዱ ለብቻው እያካፈለ ያደርጋል፡፡» 1ኛ ቆሮ.12፥8-11፡፡

እግዚአብሔር ለልጆቹ የሰጣቸው መክሊት ይህ ብቻ አይደለም፤ለአንዱ መስበክ ለሌላው የማስተማር ለሌላው የመቀደስ ለሌላው የመዘመር ለሌላው የመባረክ ለሌላው የማገልገል. . . ወዘተ መክሊቶችን ወይም ስጦታዎችን ሰጥቶአል፡፡ በፍርድ ቀን ሁሉም ሰው የሚፈረድበት በተሰጠው መክሊት ትርፍ መሠረት ነው፡፡ አንድ ሰው የሚሰጠው አንድ መክሊት ብቻ አይደለም፡፡ ሁለት ወይም ሦስት ወይም ከዚያ በላይ መክሊቶች ሊሰጡት ይችላል፡፡ እንደ ምሳሌ አድርገን ብንወስድ ለመጥምቀ መለኮት የተሰጡት መክሊቶች ብዙ ናቸው፤ በብሕትውና መኖር፣ ማጥመቅ፣ ነቢይነት፣ ንስሓ ተቀባይ ካህን፣ ስብከት፣ የሰዎችን ልብ ለጌታ የተስተካከለ መንገድ አድርጎ ማዘጋጀት፣ . . .፡፡ ዮሐንስ በተሰጡት በእነዚህ ሀብቶቹ ወይም መክሊቶቹ የብዙዎችን ልብ ወደ እግዚአብሔር በመመለስ እጅግ ስላተረፈ ጌታ ስለ እርሱ «ከሴቶች ከተወለዱት መካከል ከመጥምቁ ዮሐንስ የሚበልጥ አልተነሣም፤. . .» (ማቴ.11፥11) በማለት መስክሮለታል፡፡

ይህን ስብከት ስለ ታማኝ አገልጋይ የሚናገረውን የዐቢይ ጾም ስድስተኛ ሳምንት ስብከት ሳዘጋጅ ከሦስት ቀናት በፊት በሞት የተለዩንን በጎና ታማኝ አገልጋይ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሺኖዳ ሣልሳዊ መንፈሳዊ ሕይወት እያሰብሁ ነበር፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ለእኚህ ታላቅ አባት ብዙ መክሊቶችን ስለ ሰጧቸው በእነዚህ መክሊቶች ብዙ ሰዎችን ለእግዚአብሔር አፍርተውለታል፡፡ ይህን በማስመልከት ስለ እርሳቸው የአገልግሎት ዘመናት በሚናገር መጽሐፍ ውስጥ እንዲህ ተብሎ የተጻፉትን ቃላት አንብቤያለሁ፡- «ከምንም ነገር በላይ ቅዱስነታቸው ታታሪ ሰባኪ፣ እጅግ ጎበዝ መምህር፣ ጥበበኛ ጸሐፊ፣ ተሰጥኦ ያላቸው ገጣሚ፣ መናኝ መነኩሴ፣ የዋህ ባሕታዊ፣ የሚያነቃቁ ጳጳስ፣ ታላቅ ፓትርያርክ ናቸው፡፡ ቅዱስነታቸው አቡነ ሺኖዳ ሣልሳዊ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ምዕመናንን በስብከቶቻቸው ያነሣሡና በታላላቅ ሥራዎቻቸው የሚመሩ ብሩህ ኮከብ ናቸው፡፡» መክሊት ተቀብሎ በተቀበለው መክሊት ሌሎች መክሊቶችን የሚያተርፍ ሰው በፍርድ ቀን በኢየሱስ ክርስቶስ «መልካም፤ አንተ በጎ ታማኝም ባሪያ፤ በጥቂቱ ታምነሃል በብዙም እሾምሃለሁ፤ወደ ጌታህ ደስታ ግባ. . .» ይባላል፡፡ መክሊቱን መሬት ቆፍሮ የሚቀብረው አገልጋይ ግን በውጪ ባለው ጨለማ ውስጥ ተጥሎ በዚያ በልቅሶና ጥርስ በማፋጨት እንዲቆይ ይደረጋል፡፡

ዛሬ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ሁሉም አንድ ከሆነው ከእግዚአብሔር መንፈስ የተለያዩ ስጦታዎችን ወይም መክሊቶችን ተቀብሏል፡፡ ይሁን እንጂ ሁሉም መክሊቱን ቆፍሮ ስለ ቀበረ ለእግዚአብሔር ምንም ሊያተርፍ አልቻለም፡፡ በወንጌል ላይ የተጠቀሰው ክፉና ሃኬተኛ ባሪያ የተሰጠውን መክሊት ምንም ዓይነት ሥራ ሳይሠራበት ወይም ሳይነግድበት ወይም ሳያተርፍበት በመሬት ውስጥ ቆፍሮ በማስቀመጡና ጌታው ሲመጣ በማስረከቡ በዚህ ዘመን ከምንገኝ ሰዎች እጅጉን ይሻላል ብዬ አስባለሁ፤እኛ መክሊቶቻችንን ጠብቀን በማቆየት ለእግዚአብሔር ማስረከብ እንኳ አልቻልንምና፡፡ ዛሬ የተቀበለ ሁሉ ቀብሯል ወይም ጥሏል፡፡ አንድ የእግዚአብሔር አገልጋይ በተሰጠው የመቀደስ መክሊት መቀደስ ሲገባው የሚዘፍን ከሆነ መክሊቱን ጥሏል፡፡ አንድ የመዘመር መክሊት የተሰጠው አገልጋይ ለእግዚአብሔር መዘመር ሲገባው ሰዎችን የሚያማ ወይም የሚሳደብ ከሆነ መክሊቱን ጥሏል፡፡   ትክክለኛውን የወንጌል ትምህርት እንዲያስተምርና ሰዎችን በንስሓ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት እንዲያስገባ የማስተማር መክሊት ከኢየሱስ ክርስቶስ የተቀበለ ሰው በዚህ መክሊቱ የኑፋቄ ስብከት በመስበክ የዋህ የሆኑ ሰዎችን ወደ ሲዖል ለመምራት የሚያስተምርበት ከሆነ መክሊቱን ሙሉ ለሙሉ ጥሎታል ወይም አጥፍቶታል እንጂ አልቀበረውም፡፡ በተሰጠው የመባረክ መክሊት ወይም ሥልጣን ምዕመናንን መባረክና ኃጢአታቸውን መናዘዝ ሲገባው ለጥንቆላ ሥራ ተቀምጦ እፈርዳለሁ የሚል ከሆነ መክሊት የተባለ ክህነቱን አቃሎአታል አጥፍቷታልም እንጂ አልቀበራትም፡፡ በእግዚአብሔር መድረክ ላይ ወንጌልን መናገር ሲገባው ተራ ወሬ ወይም ፖለቲካ የሚደሰኩር ከሆነ ይህ ሰው መክሊቱን ጥሏል፡፡ ሌሎቹም እንደዚሁ፡፡ ለዚህ ነው በዚህ ዘመን ውሰጥ ያለን ሰዎች መክሊቱን ከቀበረው ሰው የምናንስ ክፉና ሃኬተኛ ሰዎች ነን እንጂ ከእርሱ የምንሻልበት ምንም ዓይነት ነገር የለንም የምንለው፡፡

እግዚአብሔር አምላክ አስቀድሞ በወንጌል እንደ ተነገረለት ለጻድቃን ሊፈርድላቸውና በኃጥአተኞች ላይ ሊፈርድባቸው ይመጣል፡፡ ከፍርዱ በፊት ሁላችንንም በሰጠን መክሊቶች መጠን ይቆጣጠረናል፡፡ አንድ መክሊት የተሰጠው ሰው ሁለትና ከዚያም በላይ ማትረፍ ይጠበቅበታል፡፡ ሁለት የተሰጠው ደግሞ ሁለት ወይም ከዚያም በላይ የሆኑ መክሊቶችን ማትረፍ ይጠበቅበታል፡፡ አምስት የተቀበልነው ደግሞ አምስትና ከዚያም የሚበልጡ መክሊቶችን ማትረፍ ይጠበቅበታል፡፡ ታዲያ እኛ ያተረፍነው ምንድር ነው? በዕርቅ ፋንታ ጠብን የምናባብስ ስለሆንን በመክሊታችን ሰዎችን አጉድለናል እንጂ ማትረፍ አልቻልንም፡፡ በመመረቅ ፋንታ የምናረገም ከሆንን መክሊታችንን ጥለናል፡፡ በመጸለይ ፋንታ ለመደባደብ የምንጋበዝ ከሆንንም የተሰጠንን መክሊት አጥፍተናል፡፡ ታዲያ የገብርኄርን ሰንበት ዛሬ ስናከብር አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተገልጦ እያንዳንዳችንን ታተርፉበት ዘንድ የሰጠኋችሁን መክሊት እስከነ ትርፉ አስረክቡኝ ቢለን ምንድር ነው የምናስረክበው? የምንሰጠውስ መልስ ምንስ የሚል መልስ ነው?

በወንጌል ላይ የተጠቀሰው ያ ሃኬተኛ ባሪያ መክሊቱን መቅበሩ ሳያንሰው  ለጌታው የሰጠው ክፉ መልስ ለከፍተኛ ቅጣት ዳርጎታል፡፡ እርሱ ለጌታው «ካልዘራህበት የምታጭድ ካልበተንህበትም የምትሰበስብ ጨካኝ ሰው መሆንህን አውቃለሁ፡፡» የሚል መልስ ነበር የሰጠው፡፡ በዘመናችን ያሉ አንዳንድ ሰዎችም ከዚህ ባሪያ ጋር የሚመሳሰል ጠባይ አላቸው፤ እነርሱ ስለ እግዚአብሔር ባሕርይ ምንም ነገር ሳያውቁ የእግዚአብሔርን ጠባይና እውቀት በእነርሱ የእውቀት ሚዛን ላይ ይሰፍራሉና፡፡ አንድ ሰው በጠና ሕመም ከታመመ ወይም ከልጆቹ አንዱ በሞት ቢለየው ወይም ንብረቱን በእሳት ቃጠሎ ቢያጣ ይህን አደጋ ያደረሰበት እግዚአብሔር እንደ ሆነ አድርጎ ለእርሱ በእርሱ ላይ ለእርሱ የማይገባ ቃላትን የሚሰነዝር ሰው አለ፡፡ ከዚህ አንጻር እነዚህ ሰዎች በእግዚአብሔር ሕልውና ላይ በመምጣት «እግዚአብሔር ቢኖር ኖሮ ይህ ሕመም ወይም አደጋ በእኔ ላይ አይደርስም ነበር፡፡» ይላሉ፡፡ ከዚህ በተጨማሪ «እግዚአብሔር እንደዚህ የጨከነብኝ ምን አድርጌው ነው;» እያሉ እግዚአብሔርን እንደ ሃኬተኛው ባሪያ ጨካኝ የሚያደርጉት ሰዎች አሉ፡፡ እግዚአብሔርን «የለህም» ወይም «ጨካኝ» ማለት ጥርስ ማፋጨት ወዳለበት ጨለማ የሚያስገባ ክፉ መልስ ነው፡፡ ሰዎች ሁለት ጊዜ ሳያስቡና አንድ ጊዜ ሳያውቁ በቸልተኝነት በእግዚአብሔር ላይ የሚሰነዝሩአቸው ቃላት ከባድ ዋጋ ያስከፍላሉ፡፡

የጻድቁ የኢዮብ ሚስት እርሷ በእግዚአብሔር ላይ በልቧ ስትሰነዝራቸው የነበሩትን ቃላት ባሏም እንደ እርሷ ይሰነዝራቸው ዘንድ «እግዚአብሔርን ስደበውና ሙት» በማለት በእርሱ ላይ ልታነሣሣው ሞክራ ነበር፡፡ ሊነቀፍ ወይም ሊወገዝ ወይም ሊኮነን የሚገባው ሰይጣን እንጂ እግዚአብሔር አይደለም፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ቸር፣ ርኅሩኅ፣ ታጋሽ፣ ይቅር ባይ፣ መዓቱ የራቀና ምሕረቱ የበዛ አምላክ ነው እንጂ «ጨካኝ» አምላክ አይደለም፡፡ እርሱ በዚህ ምድር ላይ ስንኖር ያልዘራነውን የጽድቅ ፍሬ እንድንዘራና እንድናጭድ፤ያልበተንነውንም መልካም ዘር በመበተን በፍርድ ቀን ምርቱን እንድንሰበስብ የሚፈልግ ጌታ ነው፡፡ እኛ ሠላሳ፣ ስድሳና መቶ ፍሬ በማፍራት የእነዚህ ፍሬዎችን ምርት በመሰብሰብ ሰማያዊ መንግሥቱን እንድንወርስ ስለሚፈልግ «ጨካኝ» አምላክ አይደለም፡፡ እርሱ ለሚያምኑትና ለሚታመኑት ሁሉ የሚታመን ታማኝ ጌታ ነው እንጂ የሚያምኑትን የሚክድ «ጨካኝ» ፈጣሪ አይደለም፡፡ ካልዘራበት የሚያጭድና ካልበተነበት የሚሰበስብ ሰው እንጂ እግዚአብሔር አይደለም፤ ጨካኝ፣ ከሀዲና የማይታመንም ሰው ነው፡፡

ዛሬ እግዚአብሔር በጎና ታማኝ አገልጋይ አጥቶአል፡፡ ዛሬ ቤተ ክርስቲያን የሚታመን አገልጋይ አጥታለች፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ «ሁሉ ዐመፁ በአንድነትም ረከሱ፤ በጎ ነገርን የሚሠራ የለም፤ አንድም ስንኳ የለም፡፡» (መዝ 13፡3) ተብሎ የተነገረው ለዚህ ዘመን አገልጋዮች ነው፡፡ ሰው ሁሉ ለእግዚአብሔርና ለቤተ ክርስቲያን ታማኝ ሊሆን አልቻለም፡፡ በጥቂቱ ታምኖ በብዙ ላይ ሊሾም የሚችል ሰው ስለ ጠፋ እግዚአብሔር አምላክ የሰው ያለህ እያለ ነው፤ቤተ ክርስቲያንም እንዲሁ፡፡ አገልጋዩም ሆነ ምዕመኑ በአንድነት ተባብሮ ከዳተኛ ሆኗል፡፡ ቤተ ክርስቲያን በቃሉ የሚገኝ ሰው ማግኘት ተቸግራለች፡፡ ሁሉም የተሰለፈው የቤተ ክርስቲያንን ሙዳይ በመቦጥቦጥ የግል ብልጽግናውን ለማዳበር እንጂ ለቤተ ክርስቲያን ዕድገት፣ ለምዕመናን መዳንና ወደ እግዚአብሔር መንግሥት መግባት ሲል አይደለም፡፡ እግዚአብሔር አምላክ አገልጋዮችን በቤተ ክርስቲያን ላይ የሾማቸውና የሚሾማቸው ግን ራሳቸውን፣ ቤተ ክርስቲያንንና መንጋውን ከጥፋት እንዲጠብቁ ነው፤ ሐዋ.20፥28፡፡ ለመጠበቅ ተሾሞ የሚያጠፋ ጠባቂ ዕድል ፈንታውና ዕጣ ተርታው ትሉ በማያንቀላፋበትና እሳቱ በማይጠፋበት ዘላለማዊ ሲዖል ውስጥ ነው፡፡ ይህን የሚያደርግ አገልጋይ ቅጣቱ ዘላለማዊ መሆኑን ከወዲሁ ሊያውቅ ይገባዋል፡፡ እርሱ ጌታው በዳግም ምጽአቱ እስከሚገለጥ ድረስ መንጋውን በመመገብ፣ ውኃ በማጠጣትና በማሳረፍ ፋንታ ለራሱ ብቻ የሚበላና የሚጠግብ፤ የሚጠጣና የሚሰክር፤የሚያርፍና ዘና የሚል ከሆነ ጌታው ባላሰባት ሰዓት ተገልጦ ከሁለት ይሰነጥቀዋል፤ዕድሉንም ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ባለበት ጨለማ ውስጥ ያደርግበታል፤ ማቴ. 24፥45-51፡፡ ዛሬ ጌታ አይመጣም ወይም ይዘገያል ብሎ ቤተ ክርስቲያንን በተለያያ መልኩ የሚዘርፍና እግዚአብሔርን የሚያሳዝን አገልጋይም ሆነ ተገልጋይ ከዚህ ጠባዩ ሊቆጠብ ይገባዋል፡፡  የቤተ ክርስቲያን አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ መከራ የተቀበለው ለዚህች ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ነው፡፡ በጥፊ የተመታላት፣ ርኩስ ምራቅ የተቀበለላት፣ የሾህ አክሊል የተቀዳጀላት፣ የተንገላታላትና ሞተላት ለዚህች ቤተ ክርስቲያንና ለዚህ ምዕመን ነውና አገልጋዮች በጎና ታማኞች ሊሆኑ ይገባቸዋል፡፡ የአምላካችን የእግዚአብሔር ፍቅር፣ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ እና የመንፈስ ቅዱስ ኅብረት ከእኛ ጋር ይሁን፤ አሜን፡፡

ይቆየን፡፡

በጎውን ሁሉ ለእኛ ያደረገና የሚያደርግ እግዚአብሔር ስሙ የተመሰገነ ይሁን፤አሜን፡፡

የአስቦት ገዳም በተረጋጋ ሁኔታ ላይ ይገኛል፡፡

መጋቢት 20 ቀን 2004 ዓ.ም

በኢዮብ ሥዩም


በምዕራብ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት የማገኘው የአሰቦት ቅድስት ሥላሴና የአባ ሳሙኤል ዘደብረ ወገግ ገዳም ደን በአሁኑ ጊዜ በተረጋጋ ሁኔታ ላይ እንደሚገኝ ተገለጠ፡፡

 

ያነጋገርናቸው የገዳሙ አበምኔት አባ ተክለ ማርያም እንደተናገሩት ከዚህ ቀደም የካቲት 20/2004 በገዳሙ ጥብቅ ደን ላይ የተነሣው እሳት ሙሉ በሙሉ ጠፍቷል፡፡ እሳቱን አስነስተውታል ተብለው በሚጠረጠሩ ግለሰቦች ዳግሞ እንዳይነሣ ማስተማመኛ ባይኖርም ለአሁኑ ምንም ዓይነት የእሳት ሥጋት የለም ብለዋል፡፡

በቅርቡ በተለያዩ አካባቢዎች በሞባይል ስልክ የጽሑፍ መልእክት “የአሰቦት ሥላሴ አካባቢ ደን በድጋሚ ተቃጠለ ምን ይሻለናል” በሚል ርእስ እየተሰራጨ ያለው መልእክትም ሐሰት እንደሆነና ገዳሙን እንደማይመለከትም አስተዳዳሪው ተናግረዋል፡፡

 

በገዳሙ ይዞታ የነበረውና በእሳት አደጋ የወደመውን ደን መልሶ ወደነበረበት ለመመለስና ገዳማውያኑን ለመርዳት በተለይ በማኅበረ ቅዱሳን በኩል እየተደረገ ያለውን ጥረት ያደነቁት አስተዳዳሪው በተለያየ ቦታ ያሉ ምእመናን ለገዳሙ እርዳታ እጃቸውን እንዲዘረጉም ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡

 

የጽሑፍ መልእክቶችን መሰራጨት ተከትሎ ያነጋገርናቸው ምእመናንም እንደነዚህ ዓይነት የአሉባልታ ወሬዎችና ያልተጣሩ መረጃዎች በገዳማት ላይ እየተከሠቱ ላሉ ችግሮች ዘላቂ መፍትሔ ለመስጠት የሚደረገውን ጥረት የሚያደናቅፉ ናቸው ብለዋል፡፡

 

በ13ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በአባ ሳሙኤል ዘወገግ የተመሠረተው የአሰቦት ገዳም በተደጋጋሚ እየደረሰበት ያለውን ችግር ዘላቂ መፍትሔ እንዲያገኝ ለማድረግ ማኅበረ ቅዱሳን ከተለያዩ የባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን ጥናት እያደረገ እንደሚገኝ ለማወቅ ተችሏል፡፡

የዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም ደን ቃጠሎ መጥፋቱ ተገለጠ፡፡

መጋቢት 20/2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

  • ገዳሙ አሁንም ድጋፍን ይሻል፡፡

የዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም ተከስቶ የነበረው ቃጠሎ መጥፋቱን የገዳሙ አበምኔት አባ ኢሳይያስ  ገለጹ፡፡ ገዳሙም ተጨማሪ ርዳታና ድጋፍ እንደሚያስፈልገው አሳስበዋል፡፡

ረቡዕ ጠዋት መጋቢት 12 ቀን 2004 ዓ.ም የቅዱሳን ከተማ በሚባለው የመናንያን መናኸሪያ ጭስ ይታይ የነበር ሲሆን፣ በምእመናን፣ በፌደራል ፓሊስና በኦሮሚያ ፓሊስ አባላት ጥረት በቁጥጥር ሥር እንደዋለ በቦታው የነበሩት ምእመናን ገልጸውልናል፡፡ ሁለቱ ቀናት ረቡዕና ሐሙስ በተደረገው ርብርብ በገዳሙ አንደኛው አቅጣጫ ያለው የእሳቱ መንስኤ ለዘለቄታው ሊጠፋ እንደቻለ ከቦታው የደረሰን መረጃ ያስረዳል፡፡ በቅዱሳን ከተማ ያለውን እሳት የማጥፋት ጥረት ከጠዋቱ 12፡00 የጀመረ ሲሆን ወደ 9፡30 አካባቢ ሙሉ ለሙሉ ሊጠፋ ችሏል፡፡

 

እሳቱን ለማጥፋት ጥረት በሚደረግበት ጊዜ፣ አንድ የኦሮሚያ ፖሊስ አባልና አንድ ምእመን እሳቱ ላይ በመውደቃቸው ጉዳት የደረሰባቸው ሲሆን፤ ወዲያውኑ ወደ ሕክምና እንደተወሰዱ ለማወቅ ተችሏል፡፡ የፖሊስ አባሉ አደጋ እጁ ላይ ሲደርስበት ከቢሾፍቱ የመጣው ምእመን እግሩ ላይ ጉዳት ደርሶበታል፡፡

 

በተያያዘም የገዳሙን ችግር በዘላቂነት ለመፍታት ከሚመለከታቸው ከጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ተወካዮችና ከመስተዳድር አካላት ጋር በገደሙ አጠቃላይ ችግሮች ዙሪያ በስፋት መነጋገራቸውን አባ ኢሳይያስ ተናግረዋል፡፡

 

የመንገድና የውሃ ችግር በገዳሙ ላይ ጎልተው የሚታዩ ፈተናዎች መሆናቸውንና ይህንንም ለመፍታት የሁሉም ርብርብ እንደሚጠይቅ ያሳሰቡት አበምኔቱ ገዳሙ ያለውን የምግብ ፍጆታ በቃጠሎው ለተሳተፉ ምእመናን በማዋሉ ሊሟጠጥ ችሏል፡፡ በዚህም መሠረት ለመነኮሳቱ የሚሆን ቀለብ ባለመኖሩና ጊዜያዊ ችግር እንዳይገጥማቸው በማሰብ በማኅበረ ቅዱሳን ዋናው ማእከል አማካይነት ከበጎ አድራጊ ምእመናን ያገኘውን የበሶ፣ የስኳርና የውኃ ልገሳ በትላንትናው ዕለት ወደ ገዳሙ በመውሰድ ለሚመለከታቸው አባቶች አስረክቧል፡፡

 

በቢሾፍቱ የማኅበረ ቅዱሳን ማእከል አባላት፣ በቢሾፍቱ ደብረ መዊእ ቅዱስ ሚካኤልና በቅዱስ ሩፋኤል ቤተ ክርስቲያንም ገዳሙ ያለበትን ጊዜያዊ የውኃ ችግር ለመቅረፍ እንዲቻል ምእመናንን በማስተባበር ብዛት ያላቸው የውኃ ጀሪካኖችን በመሰብሰብ ውኃ በመሙላት ወደ ገዳሙ በማመላለስ ላይ ይገኛሉ፡፡ በተጨማሪም በጎ አድራጊ ምእመናን ገንዘብ በማሰባሰብ ለሁሉም አብያተ ክርስቲያናት ጥራጥሬና እህል በመግዛት ወደ ገዳሙ ለመውሰድ በዝግጅት ላይ እንደሚገኙ ገልጸዋል፡፡

 

ከጠቅላይ ቤተ ክህነት እስከ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያናት፣ የፌደራል ፓሊስ፣ የኦሮሚያ ፓሊስ፣ የአየር ኀይል፣ ማኅበራትና ምእመናን የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ፍቅር አስገድዷቸው ከሩቅም፣ ከቅርብም ወደ ገዳሙ በመገስገስ ቃጠሎውን ለማጥፋት ላደረጉት ከፍተኛ ርብርብ አበምኔቱ ምስጋናቸውን በራሳቸውና በማኅበረ መነኮሳቱ ስም አቅርበዋል፡፡