የዝቋላ ደን ቃጠሎ ተጨማሪ እርዳታ እንደሚያስፈልገው ተገለጠ፡፡

መጋቢት 11/2004 ዓ.ም

በተ/ሥላሴ ጸጋ ኪሮስ

የዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም ደን ቃጠሎ ተጨማሪ እርዳታ እንደሚያስፈልገው ተገለጠ፡፡

በቦታው የተገኙት የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ ሊቀ ትጉሃን ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ሥዩም እንደገለጡልን በቦታው በርካታ ምእመናን ተገኝተው እሳቱን ለማጥፋት ጥረት ቢያደርጉም በአስቸጋሪው የአየር ጠባይ የተነሣ ፍህሙ እየተነሳ እንደገና እንዲያገረሽ ስለሚያደርገው ከፍ ያለ እርዳታ እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል፡፡

ከመንገዱ አስቸጋሪነት እና ከፀሐዩ ግለት አንፃር ከእሳቱ ቃጠሎ ጋር ለሚታገሉ ምእመናንም  የጥም ማስታገሻ የሚሆን ውሃ በመኪና ለማድረስ እንዳልተቻለ ከስፍራው የደወሉልን ምእመናን ገልጠውልናል፡፡

በአሁኑ ወቅት የእሳት አደጋው አርብ ረቡዕ በሚባለው ቦታ እየነደደ እንደሆነና የገዳሙን ደን የምሥራቁን ክፍል እየጨረሰ ወደ ደቡብ አቅጣጫ እየዞረ እንደሆነ ታውቋል፡፡ በአካባቢው ያለው ማኅበረሰብ ትብብር አነስተኛ እንደሆነባቸው ያልሸሸጉት ምእመናኑ፣ ለእርዳታ የሚመጡ ምእመናንም በተቻላቸው አቅም መጥረቢያ፣ አካፋና መቆፈሪያ ይዘው ቢመጡና ምእመናኑም እሳቱን ለማጥፋት አቅም ያላቸው ቢሆኑ ይመረጣል ብለዋል፡፡

በተጨማሪም በቅርብ ሰዓት በደረሰን መረጃ መሠረት፣ ከሌሊቱ 8፡00 አካባቢ እሳት ወደሚነድበት አካባቢ ለቅኝት የተጓዙ ምእመናን መሬት ላይ ያለው ፍሕም ነፋሱ በመራው አቅጣጫ እየተነሳ እንደሚያቀጣጥል መመልከታቸውንና ከቦታው አስቸጋሪነት አንፃር ምንም ማድረግ እንዳልቻሉ ተናግረዋል፡፡

ለእርዳታ የተጓዘውን ምእመን የማስተናገድ ሸክም በገዳሙ ጫንቃ ላይ እንደወደቀ መነኮሳቱ የተናገሩ ሲሆን፣ ከጊዜ በኋላ ከዐቅም በላይ ሊሆን ስለሚችል ስንቅ በማቅረብ በኩልም ቢሆን ሊተባበሩ የሚችሉ ምእመናንን እርዳታ እንደሚሹ ገልጠዋል፡፡

አምላክ ገብረ መንፈስ ቅዱስ በይቅርታው ይታደገን!!!

በዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም የደን ቃጠሎ በባሰ ሁኔታ ላይ ይገኛል!

መጋቢት 10/2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ


እሳት ወይስ መአት?


በዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም የደን ቃጠሎ በባሰ ሁኔታ ይገኛል፡፡ ቅዳሜ መጋቢት 8/2004 ዓ.ም. ከቀኑ 6፡00 በኋላ ልዩ ስሙ አዱላላ ከሚባለው አቅጣጫ የተቀሰቀሰው ቃጠሎ በመነኮሳትና በአካባቢው ምእመናን ለማጥፋት ከፍተኛ ጥረት  እያደረጉ እንደሚገኙና ከደብረ ዘይት የአየር ኀይል አባላት ትላንት ምሽት መጥተው እገዛ ለማድረግ ጥረት ማድረጋቸውን የገዳሙ ጸሐፊ አባ ወ/ሩፋኤል ቢገልጹም መፍትሔ እንዳልተገኘ ታውቋል፡፡

 

የቃጠሎው መንስኤ ለማወቅ ያልተቻለ ሲሆን “የቅዱሳን ከተማ” የተሰኘው የአባቶች የጸሎት ሥፍራ በከፍተኛ ሁኔታ በመቃጠል ላይ እንደሚገኝና በሥፍራው ውኃ የሌለ በመሆኑ ቃጠሎውን ለማጥፋት አፈሩን በመቆፈርና በመበተን እንጨቶችን በመቁረጥና በቅጠል በማጥፋት ርብርቡ የቀጠለ ቢሆንም ቃጠሎውን መግታት እንዳልተቻለ አባ ወልደ ሩፋኤል ጨምረው ገልጸዋል፡፡ ወደ ጸበሉ ቦታ እንዳይደርስ ጥረት እየተደረገ ሲሆን ምእመናን ከተለያዩ አካባቢዎች ወደ ገዳሙ በመሔድ ቃጠሎውን ለማጥፋት እየተረባረቡ ይገኛሉ፡፡ የገዳሙ ጸሐፊ አባ ወልደ ሩፋኤል ቃጠሎው ያደረሰው ጉዳት ከፍተኛ በመሆኑ መጠኑን ለመግለጽ መቸገራቸውንና ለመንግሥት አካላትና ለምእመናን የድረሱልን ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡ ከቅርብ ጊዜ ጀምሮ ተመሳሳይ ቃጠሎ በተለያዩ ቤተ ክርስቲያናት ላይ እየደረሰ በመሆኑ “እሳት ወይስ መአት?! በማለት በጭንቀትና በስጋት ምእመናን እየገለጹ ይገኛሉ፡፡

 

በ2000 ዓ.ም. በዚሁ ገዳም ቃጠሎ ተከስቶ እንደነበር የሚታወስ ሲሆን በቅርቡም በጎንደር የሰለስቱ ምእት መጻሕፍተ መነኮሳት ጉባኤ ቤት፣ እንዲሁም የጥንታዊው የሥላሴ ቤተ ክርስቲያን የቅኔ ትምህርት ቤት ቃጠሎ የደረሰባቸው ሲሆን በምዕራብ ሐረርጌ የሚገኘው የአሰቦት ገዳም ደን ላይ ከፍተኛ ጉዳት መድረሱም ይታወቃል፡፡

 

የዝቋላ የሰኞ መጋቢት 10 ቀን 2004 ዓ.ም. ውሎ

ቃጠሎው እጅግ አሳሳቢ  ሆኗል፡፡


ከጧት ጀምሮ ምእመናን ከደብረ ዘይት፣ ከአዲስ አበባ ከተለያዩ መሥሪያ ቤቶች የተውጣጡ የቤተ ክርስቲያን ልጆች፣ በማኅበረ ቅዱሳን የሚመራው የዩኒቨርሲቲዎች የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች፣ የሰንበት ትምህርት ቤቶች አባላት ቃጠሎውን ለማጥፋት ቦታው ድረስ ተንቀሳቅሰዋል፡፡ ከገዳሙ በደረሰን መረጃ መሠረት እስከ ቀኑ 12፡00 ሰዓት ድረስ ቃጠሎው በፀሐይና በንፋስ በመታገዝ ከፍተኛ ውድመት እያደረሰ ይገኛል፡፡ መነኮሳቱ ለኦሮሚያ ፖሊስ፣ ለፌደራል ፖሊስና ለአየር ኀይል እንዲሁም ለምእመናን የድረሱልን ጥሪ በማሰማት ላይ ይገኛሉ፡፡ በተለይም ቦታው እጅግ አስቸጋሪ በመሆኑ ውኃ ማግኘት ባለመቻሉ የደኑን ውድመት እያባባሰው ስለሚገኝ ውኃ የሚያመላልሱ ቦቴ መኪናዎች ያሏቸው ምእመናን ውኃ በማመላለስ እንዲደርሱላቸው በመማጸን ላይ ናቸው፡፡

 

ከተለያዩ አካባቢዎች የተንቀሳቀሱት ምእመናን ከአስቸጋሪ ጉዞ በኋላ ከቀኑ 10፡00 ሰዓት ላይ ቦታው የደረሰ ሲሆን ለማጥፋት ከፍተኛ ጥረት በማድረግ ላይ ይገኛሉ፡፡ ይህንን ዜና እስካጠናቀርንበት 12፡00 ሰዓት ድረስ ቃጠሎው እንዳልጠፋና ከሌላ አቅጣጫ ሌላ አዲስ ቃጠሎ መቀስቀሱን በቦታው ከሚገኙ ምእመናን ለመረዳት ችለናል፡፡ ቃጠሎው በዚሁ ከቀጠለ ከፍተኛ የደን ሀብት ያለበት ቦታ መያዙ እንደማይቀር ስጋታቸውን በመግለጽ ላይ ናቸው፡፡

 

በቃጠሎ ጉዳት የደረሰባቸው ምእመናን እንደሚገኙ ከቦታው የደረሰን መረጃ የሚያመለክት ሲሆን በከፍተኛ ጥምና ረሃብ ላይ ለሚገኙ ምእመናን ውኃና ምግብ እንደሚያስፈልጋቸው ጭምር ገልጸዋል፡፡

የዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም ደን እየተቃጠለ ነው፤ የምእመናንን እገዛ ይሻል፡፡

መጋቢት 10/2004 ዓ.ም.


በተ/ሥላሴ ጸጋ ኪሮስ


ቅዳሜ መጋቢት 8 ቀን 2004 ዓ.ም ከቀኑ 6፡00 በኋላ የጀመረው የገዳሙ ቃጠሎ እየተባባሰ እንደሆነ የገለጹልን ያነጋገርናቸው የገዳሙ መነኮሳት እሳቱን ለማጥፋት የምእመናንን እርዳታ እንደሚሻ አሳስበዋል፡፡

 

አያይዘውም ለእርዳታ የሚመጡ ምእመናን ስንቅ እንዲይዙና በውኃ ጥም እንዳይቸገሩ ከቻሉ ውኃ እንዲይዙ፤ ቦቴ መኪና ያላቸውም እንዲተባበሩ ጠይቀዋል፡፡

 

በአሁኑ ወቅት ምእመናን ከደብረ ዘይትና አዲስ አበባ ዙሪያ ወደ ገዳሙ ለእርዳታ እየተጓዙ እንደሆነ ያገኘናቸው መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡

 

ዝርዝር ሁኔታውን በቀጣዩ እናቀርባለን፡፡

አምላከ ገብረ መንፈስ ቅዱስ በምሕረቱ ይታረቀን፡፡

ቦጅ ትጮሀለች!

መጋቢት 10/2004 ዓ.ም.

በዲ/ን ኅሩይ ባየ

ኘሮቴስታንቲዝም በምዕራቡ ዓለም ተጸንሶ ተወልዶና አድጐ የጐለበተ ከካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ያፈነገጠ የእምነት ተቋም ነው፡፡ ተወልዶ ባደገበት ሀገር ይዞታውን አንሰራፍቶ ለጊዜው የዘለቀው ኘሮቴስታንቲዝም በሀገሩ ባይተዋር ሲሆን “ጅብ ባለወቁት ሀገር ቁርበት አንጥፉልኝ አለ” እንደሚባለው ወደ ድሃ ሀገሮች በመዝመት ባንድ እጁ ዳቦ በአንድ እጁ እርካሽ እምነቱን ይዞ ገባ፡፡ በዚህ እኩይ ተልዕኰ የተወረሩ በርካታ የአፍሪካ ሀገሮች ባሕላቸውን ትተው፣ ቋንቋቸውን እረስተው ዘመን አመጣሽ የሆነውን አዲስ እምነት ለመቀበል ተገደዋል፡፡

{gallery count=1 width=350 height=300 counter=1 links=0 alignment=center animation=3000}bogi{/gallery}

ሀገራችን ኢትዮጵያ ነፃነቷን አስጠብቃ በጠላት እጅ ሳትወድቅ አንድነቷ ተከብሮ የኖረች ስሟ በቅዱስ መጽሐፍ ተደጋግሞ የተነሣ ቅድስት ሀገር ናት፡፡ ግማደ መስቀሉ ያረፈባት ታቦተ ጽዮን የከተመባት ውቅር አብያተ ክርስቲያናት የታነጹባት ያለመታከት ስመ እግዚአብሔር የሚጠራባት ልዩ ሀገር ናት፡፡ በባእዳን እጅ አለመውደቋ በቀኝ ግዥ አለመያዟ የእግር እሳት የሆነባቸው ምዕራባውያን ድንበሯን ጥሰው መግባት ባይችሉም የአእምሮ ቅኝ ግዛታቸውን አላቋረጡም፡፡

 

በዚች ሀገር ውስጥ ይህ ዘመቻ በስፋት ከሚካሔድባቸው ቦታዎች አንዱ ሰፊ የሆነው የኦሮሚያ ክልል ነው፡፡

 

ቦጅ ቅድስት ማርያም ጠላቶቿን ስታስታውስ

የፕሮቴስታንቱን ተፅዕኖ ለመግታት ማኅበረ ቅዱሳን ባዘጋጀው የካህናት ሥልጠና የካቲት 17 ቀን 2004ዓ.ም ረፋዱ ላይ በቤተ ክርስቲያኗ ቅጽር ግቢ ስንገኝ ማንም ሰውbogi 1 አልነበረም፡፡ በቅጽሩ ጥግ ለጥግ ያረጁ የመካነ መቃብር ሐውልቶች ይታያሉ፡፡ በቤተ ክርስቲያኗ ፊት ለፊት በስተቀኝ በኩል ፈንጠር ብለው በክብር የተሠሩ አጥራቸው የተከበረ የቄስ ገብረ ኤዎስጣቴዎስ ዘመስቀል /1865-1905/፣ የአቶ ዳንኤል ዲባባ /1966-1904/ እና የአቶ ገብረ ኢየሱስ ተስፋዬ /12877-1925ዓ.ም./ መካነ መቃብር ይታያል፡፡ እነዚህ ሐውልቶች ለኘሮቴስታንት ቤተ ክርስቲያን ባለ ውለታ ለሆኑት ሦስት ግለሰቦች ለመታሰቢያ እንዲሆን የተሠራ ሐውልት እንደሆነ ነዋሪዎች አጫውተውናል፡፡ በተለይ ከሦስቱ ሰዎች አንዱ ቄስ ገብረ ኤዎስጣቴዎስ በርካታ ካሕናትን አስኮብልሎ የእኛ ቤተ ክርቲያን እንድትዘጋ ስላደረገ ኘሮቴስታንቱ ስሙን ይዘክሩታል፡፡ በዚች ጠባብ ከተማ 130 ዓመታት ያስቆጠረች የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ቤተክርስቲያን ትገኛለች፡፡ በከተማዋ ያደረግነው ቆይታ ከሀገረ ስብከቱ ስራ አስኪያጅ ከመጋቤ ሀዲስ ሀዲስ ዓለማየሁ እና ከወረዳው ቤተ ክህነት ሊቀ ካህናት ምሥጢሩ ዘለቀ ጋር ነበርን፡፡

 

በቦጂ ድርመጂ ወረዳ ዐሥር አድባራት ይገኛሉ፡፡ ከሕዝቡ በመቶኛ ዘጠና አምስት በመቶ የኘሮቴስታንት እምነት ተከታዮች እንደሆኑ ይገመታል፡፡ በጥንታዊነቷ የምትታወቀው የቦጂ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስትያን አንድ መቶ ሠላሳኛ ዓመቷን የምታከብረው የፊታችን ግንቦት 1 ቀን 2004 ዓ.ም ነው፡፡

 

bogi 2ሊቀ ካህናት ምሥጢሩ ስለ ቦጂ ቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን ታሪክ በአጭሩ ነግረውናል፡፡ እኛም እድሜ ጠገብነቷ አስደምሞን ልቡናችን በቤተ ክርስቲያኗ ታሪክ መዋለል ዓይኖቻችን በሕንፃዋ መንቀዋለል ጀመሩ፡፡ ከወፍ ድምጽ በቀር ምንም የማይሰማባት ቤተ ክርስቲያን ናት ማህሌቱ፣ቅዳሴው፣ጸሎተ እጣኑ ከተቋረጠ ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ ይህቺ ደብር የወላድ መካን የሆነች ካሕናቷ በኘሮቴስታንት ሰባኪያን የተወሰዱባት ቤተ ክርቲያን ናት፡፡ በልጆቿ መጥፋት ያዘነችው ቦጂ ቅድስት ማርያም ልጆቼን! እያለች ትጮኸለች፡፡

 

ተሐድሶ በዚያን ዘመንም

ከቦታው ያገኘነው ታሪክ እንደሚያስረዳው በ1890 ዓ.ም ከሲዊዲን ሀገር የመጡ የኘሮቴስታንት እምነት ሰባኪዎች ፊት ለፊት ከሚታየው ከርከር ተራራ ጸሎት ቤት ከፈቱ፡፡ እነዚህ ነጭ ሰባኪያን የመጀመሪያ ሥራቸው ያደረጉት የእኛን ቤተ ክርስቲያን ካሕናት መለወጥ ነበር፡፡ ኘሮቴስታንቶች በኢትዮጵያ ያደረጉት ተልእኮ መሠረት የተጣለው በዚህች ከተማ ነው፡፡ የመካነ ኢየሱስ ምዕራብ ሲኖዶስ ጽሕፈት ቤት የሚገኘው በዚህች ከተማ ነው፡፡

 

በቤተ ክርስቲያኗ ያኔ በርካታ ካህናትና ዲያቆናትና ነበሩ፡፡ ከካህናቱ መካከል ከኤርትራ ሀገር የመጣ ቄስ ገብረ ኤዎስጣቴዎስ የሚባል “ካህን” ነበር፡፡ መናፍቃኑ ይህን ቄስ ቀስ በቀስ ሰብከው ከለወጡት በኋላ አሠልጥነው የውስጥ ዘመቻቸውን አቀጣጠሉ፡፡

 

ቄስ ገብረ ኤዎስጣቴዎስ ለበርካታ ጊዜያት ራሱን ሰውሮ ጠዋት በእኛ ደብር እየቀደሰ ከሰዓት በኃላ በመናፍቃኑ አዳራሽ እየተገኘ የመናፍቃኑን ተልእኮ ይፈጽማል፡፡ /ምን አልባት ተሐድሶዎቹ የዚያን ጊዜም እንቅስቃሴያቸውን ጀምረው ይሆን?/ ይህ ቄስ ለ15 ዓመታት በዚህች ደብር ሲያገለግል የነበረ ሰው ነው፡፡ በኋላ ወደ አምስት የሚሆኑ ካህናትን ሰብኮ ወደ መናፍቃኑ አንድነት ቀላቀላቸው፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ቤተ ክርስቲያኗ በካህናት እጥረት አገልግሎቷ ታጐለ፡፡ አሁን ቤተ ክርስቲያኗ  ልጆቿ የሉም፡፡ የከተማዋ ነዋሪዎች ምን ያህል እንደሆኑ ትክክለኛ ቁጥራቸውን መናገር ባይቻልም የኦርቶዶክስ እምነት ተከታዮች 14 የሚሆኑት ብቻ ናቸው፡፡ ከእነዚህ አባወራዎች አብዛኛዎቹ ሚስቶቻቸው ኘሮቴስታንት የሆኑባቸው አባቶች ናቸው፡፡ በሃይማኖት ተለያይቶ በአንድ ቤት መኖር ከባድ ቢሆንም አማራጭ ስለጠፋ አብረው ለመኖር እንደተገደዱ አባወራዎቹ ይናገራሉ፡፡

 

ሚስቶቻቸው በኘሮቴስታንቶች ተሰብከው ከተነጠቁባቸው አባወራዎች መካከል አቶ ተሰማ ደበበ አንዱ ናቸው፡፡ በኦሮምኛ የነገሩንን ወደ አማርኛ እነዲህ ተርጉመነዋል፡፡ “ ወደ ኘሮቴስታንት እምነት ከሔዱት ሰዎች በጣም በርካታ ቁጥር ያላቸው ከዚህች ቤተ ክርስቲያን የወጡ ምእመናን ናቸው፡፡ ይህቺ ቤተ ክርቲያን ወጣት የሚባል ተተኪ የላትም፤ ሚስቶቻችን ወደ ቀድሞ የኦርቶዶክስ እምነታቸው እንዲመለሱ ጥረት ብናደርግም እሺ ሊሉን አልቻሉም፡፡ አሁንም የቻልነውን ሁሉ እናደርጋለን፤ ማን ያውቃል አንድ ቀን ሊመለሱ ይችላሉ” በማለት ተስፋቸውን ነግረውናል፡፡

 

ቤተ ክርስቲያኗ ለ4 ዓመታት ያህል ተዘግታ መኖሯን የገለጠልን አንድ ዲያቆን ከ1982 ጀምሮ ዲቁና ተቀብሎ እያገለገለ ቢሆንም ካለበት bogi 4የመንግሥት ሥራ ጋር አጣጥሞ አገልግሎቱን አጠናክሮ መቀጠል እንዳልቻለ ገልጦልናል፡፡ የከተማዋ ነዋሪዎችም ሥራ ለማግኘትና በኘሮጀክት ታቅፈው የእለት ኑሮአቸውን ለመግፋት ሳይወዱ በግድ ወደ ኘሮቴስታንት እምነት ለመሔድ እንደሚገደዱ ነዋሪዎች ይገልጣሉ፡፡

 

በአሁኑ ሰዓት የቤተ ክርስትያኗን ቁልፍ ይዞ ካህንም ፣ዲያቆንም፣ ሰንበት ተመማሪም፣ አስተማሪም፤ ጠባቂም ሆኖ የሚያገለግለው ዲያቆን አበበ ኅሩይ በኘሮቴስታንቱ የደረሰባቸውን  ከፍተኛ ጉዳት እንዲህ ይናገራል፡፡ “እኔ እንደማስታውሰው በ1988 ዓ.ም የተወሰኑ የሰንበት ት/ቤት ተማሪዎች ነበሩ፡፡ በዚያን ወቅት የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት የሚያስተምር ሰባኪ ስላልነበረን የነበሩት ምእመናን በአንድ ላይ ተሟጥጠው ወደ ኘሮቴስታንቱ የጸሎት ቤት ገቡ፡፡ ሌላው ይቅርና የቤተክርስቲያኗ ቁልፍ ያዥ የነበረው ቄስ አዳሜ ገብረ ወልድ በጠዋት መጥቶ ‘በል ይህን የቤተ ክርስቲያን ቁልፍ ተረከበኝ ወደ ኘሮቴስታን የጸሎት ቤት መሔዴ ነው’ ብሎ ጥሎልኝ ሔደ፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ቁልፉን ይዤዋለሁ፡፡ በአጥቢያዋ የሚኖሩ 14 የሚሆኑ ምእመናን አቅመ ደካሞች ናቸው፡፡ እነሱ ሲያልፉ ማን እንደሚተካ ሳስበው ይጨንቀኛል፡፡” ይላል፡፡

 

መፍትሔ

የአከባቢው ተጽእኖ የኘሮቴስታንቱ ድባብ የዋጣቸው በርካታ ወገኖቻችን አሉ፡፡ስለ ኦርቶዶክስ ሃይማኖት ሳያውቁ በጭፍኑ የኮበለሉ ብዙ ነፍሳት አሉ፡፡ በቅርቡ በተደረጉ ሁለት መንፈሳዊ ጉዞዎች ባለፈው ክረምት ለ2 ወራት በተደረገው ጠንካራ የስብከተ ወንጌል እንቅስቃሴ አርባ ሁለት ሰዎች ወደ ኦርቶዶክስ እምነታቸው እንደተመለሱ የምዕራብ ወለጋ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ ያብራራሉ፡፡ የአካባቢው ፕሮቴስታንታዊ ተጽእኖ ከባድ መሆኑ ስለታመነበት የካህናት ሥልጠና እንዲሰጥ ታምኖበታል፡፡ ይህ በመሆኑ በማኅበረ ቅዱሳን ዋናው ማእከል አዘጋጅነት በምዕራብ ወለጋ ሀገረ ስብከት በጊምቢ ከተማ መንበረ ጵጵስና ከየካቲት 12-16 ቀን 2004 ዓ.ም. ከአሶሳ፣ ከቄለም እና ምዕራብ ወለጋ አህጉረ ስብከት ለተውጣጡ 150 ካህናት ሥልጠና ተሰጥቷል፡፡ በብፁዕ አቡነ ሄኖክ ጸሎተ ቡራኬ የተጀመረው የካህናት ሥልጠና በነገረ ሃይማኖት መግቢያ፣ በአእማደ ምሥጢራት፣ በነገረ ድኅነት፣ በነገረ ቅዱሳን፣ በአጠቃላይ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ፣ በሕግጋተ እግዚአብሔር፣ በትምህርተ ኖሎት እና በወቅታዊ የተሐድሶ እንቅስቃሴ ላይ ያተኮረ ትምህርት ተሰጥቷል፡፡

 

በስልጠናው ማጠናቀቂያ ዕለት ካህናቱ በሰጡት አስተያየት የተሰጠው ሥልጠና ለቀጣዩ የስብከተ ወንጌል አገልግሎታቸው ከፍተኛ ሚና እንዳለው ገልጠዋል፡፡ በተለይ በምዕራብ ወለጋ የሚታየውን የተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴ ለመፍታት በንቃትና በትጋት እንደሚያገለግሉ ተናግረዋል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን የሰጠው ይህ ሥልጠና እጅግ ጠቃሚና ወቅታዊ በመሆኑ ለወደፊቱ ተደጋጋሚ የሆነ የካህናት ሥልጠና ቢደረግ በቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ አገልግሎት ከፍተኛ የሆነ ስኬት ሊመጣ እንደሚችል ካህናቱ አስተውቀዋል፡፡

 

የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ መጋቤ ሐዲስ ሐዲስ ዓለማየሁ፣ የወረዳው ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ካህናት ምሥጢሩ እና በዕለቱ ያገኘናቸው ምእመናን እንዲሆንላቸው የሚመኙትን እየተማጸኑ ነግረውናል፡፡

 

  1. በዚህች ከተማ መናፍቃኑ መሠረታቸውን ጥለው የእኛን ቤተ ክርስቲያን እና ምእመናን አስከልክለውብናል፡፡ የነገሩን ምንጭ ለማድረቅ በዚህች ከተማ የተጠና ፕሮጀክት ቢጀመር በሥራ እጦት እየተጨነቁ ሃይማኖታቸውን ጥለው የሔዱት ወገኖቻችን ሊመለሱ ይችላሉ፡፡
  2. በኦሮምኛ ቋንቋ የሚያስተምሩ ሰባኪያነ ወንጌል ቢመደቡልን
  3. ተተኪ ወጣቶችን የሚያስተምሩ የአብነት መምህራን ቢቀጠሩልን እና
  4. በመጪው ግንቦት 1 ቀን 2004 ዓ.ም. ለምናከብረው ዓመታዊ በዓል ሰፊ ጉባኤ እንዲደረግልን ለመምህራን ትራንስፓርት፣ ለድምጽ ማጉያ፣ እና ለአንዳንድ ወጪዎች የሚሆን ገንዘብ የሚደግፉን በጎ አድራጊ ምእመናን ቢገኙ ከፍተኛ የሆነ ለውጥ ይመጣል፡፡ የስብከተ ወንጌል ጉባኤ በዓመት አንድ ጊዜ ብቻ ሳይሆን በተከታታይ የሚሰጥ ከሆነ ባለፈው ጊዜ የተመለሱት ምእመናን በእምነታቸው ይጸናሉ ያልተመለሱትም ወደ እናት ቤተ ክርስቲያናቸው ይመጣሉ ይላሉ፡፡

 

bogi 5ቦጂ ቅድስት ማርያም ጥንታዊት ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ ያጣቻቸውን ልጆች መልሳ ለማግኝት በሯን ከፍታ ትጠብቃለች፤ ተከታታይ ጉባዔያት ቢካሔዱ በአፍ መፍቻ ቋንቋቸው የሚያስተምራቸው ሰባኬ ወንጌል ቢመደብላቸው የጠፉት ነፍሳት ሊመለሱ እንደሚችሉ ምእመናን በመሉ ተስፋ ይናገራሉ፡፡ እኛም ታሪክ ተቀይሮ መናፍቃኑ መሠረት ከጣሉበት ቦታ አንድ ለውጥ ይመጣ ይሆን? የሚለውን ጥያቄ በውስጣችን ይዘን ተመልሰናል ሕንጻ ቤተ ክርስቲያንን ከመገንባት ሕንጻ እግዚአብሔር ሰውን ማነጽ ይበልጣል፡፡ የጠፉት በጐች ወደ በረታቻው ካልተመለሱ እዳው የቤተክርስቲያን መሆኑ አያጠያይቅም ስለዚህ ባለ ድርሻ አካላት የምንችለውን ሁሉ እንድናደርግ ቦጂ ትጮሀለች፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

baba shenouda

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሲኖዳ 3ኛ አረፉ፡፡

በተ/ሥላሴ ጸጋ ኪሮስ
የቅብጥ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሲኖዳ 3ኛ አረፉ፡፡
የቅብጥ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ማርቆስ መንበር 117ኛ ፓትርያርክ ብፁዕ አቡነ ሲኖዳ ትናንት መጋቢት 8 ቀን 2004 ዓ.ም. አረፉ፡፡
ቢቢሲ የግብፅን ብሔራዊ የቴሌቪዥን ጣቢያ ጠቅሶ እንደዘገበው ቅዱስነታቸው በካንሰር ሕመም ምክንያት በ88 ዓመታቸው አርፈዋል፡፡
በሰሜናዊ ግብፅ፣ አስዩት ውስጥ ሐምሌ 27 ቀን 1915 ዓ.ም ሲወለዱ ናዚር ጋይድ የሚል መጠሪያ ከቤተሰባቸው የተሰጣቸው ቅዱስነታቸው፣  ቅስናን ሲቀበሉ አባ እንጦንስ ተብለው ይጠሩ የነበር ሲሆን አቡነ ሲኖዳ የተባሉት በ1955 ዓ.ም የክርስትና ትምህርት ኤጲስ ቆጶስ ተብለው በተሸሙበት ወቅት ነበር፡፡
ቅዱስነታቸው አቡነ ሲኖዳ የቅብጥ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን 117ኛ ፓትርያርክ ሆነው በወንጌላዊው ቅዱስ ማርቆስ መንበር ላይ የተሾሙት ከተአምር ሠሪው ፓትርያርክ ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቄርሎስ 6ኛ በኋላ ኅዳር 4 ቀን በ1964 ዓ.ም ነበር፡፡፡
ቅዱስነታቸው ከ5ኛው ክፍለ ዘመን በኋላ የቲዎሎጂ ሴሚናሪ ዲን የሆኑ የመጀመሪያው ፓትርያርክ ሲሆኑ በአገልግሎት ዘመናቸው ከ3 የአሜሪካን እንዲሁም ከ1 የጀርመን ዩኒቨርስቲ የክብር ዶክትሬት ተቀብለዋል፡፡
ቅዱስነታቸው ሕይወታቸው የትሕርምት፣ የጸሎትና የአገልግሎት እንደነበር የሕይወት ታሪካቸውን የሚዘግቡ ድርሳናት የሚገልጹ ሲሆን ባለፉት 20 ዓመታት የዓለምን ሕዝብ ያስተማሩባቸው 80 መጻሕፍትን ደራሲና የቤተ ክርስቲያኗ ኦፊሴላዊ መጽሔት ኤል-ኬራዛ ዋና አዘጋጅ ነበሩ፡፡
በግብፅ ርዕሰ ብሔር አንዋር ሳዳት ጊዜ አክራሪ ሙስሊሞች በክርስቲያኖች ላይ የሚያደርሱት ጥቃት መጨመርና መፋፋም ያሳሰባቸው ቅዱስነታቸው በመንግሥቱ ላይ ባነሱት ተቃውሞ፣ ለ40 ወራት ከመንጋዎቻቸው ተለይተው ወደ ቅዱስ ቢሶይ ገዳም ተግዘው የአባቶቻቸውን በረከት ተካፍለው እንደነበር የሚታወቅ ሲሆን በኋለኛው መሪ ሆስኒ ሙባረክ ዘመን ወደ መንበራቸው ተመለሰው እስከ ዛሬ ድረስ ጠቦቶችን ሲጠብቁ፣ ግልገሎችና በጎችን ሲያሰማሩ ቆይተው አርፈዋል፡፡
በግብፅ ሕዝብ በተለይም በኦርቶዶክሳውያን ዘንድ ተወዳጅ አባት እንደሆኑ የሚነገርላቸው ቅዱስነታቸው በግብፃውያን ክርስቲያኖችና ሙስሊሞች መካከል ያለውን ግንኙነት ለማሻሻልና ሰላማዊ ለማድርግ ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይሉ እንደደከሙ ይመሠከርላቸዋል፡፡
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሲኖዳ ኢትዮጵያን  ሁለት ጊዜ የጎበኙ ሲሆን ከመጀመሪያው ጉብኝታቸው 30 ዓመታት በኋላ በ2000 ዓ.ም ሚያዝያ ወር ላይ ያደረጉት ጉበኝት የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነበር፡፡
ጸሎታቸው ከሁላችን ጋር ይሁን፣ ማኅበራችን ማኅበረ ቅዱሳን ለግብፃዉያን ወንድም እህቶቻችንና ቅዱስነታቸውን ለሚወዱ ሁሉ መጽናናትን ይመኛል፡፡
መጋቢት 9/2004 ዓ.ም.

በተ/ሥላሴ ጸጋ ኪሮስ

የቅብጥ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሲኖዳ 3ኛ ዐረፉ፡፡ የቤተ ክርስቲያኗ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳትና የቅዱስ ማርቆስ መንበር 117ኛ ፓትርያርክ የቅዱስነታቸው ዕረፍት የታወቀው ትናንት መጋቢት 8 ቀን 2004 ዓ.ም. ነበር፡፡

 

ቢቢሲ የግብፅን ብሔራዊ የቴሌቪዥን ጣቢያ ጠቅሶ እንደዘገበው ቅዱስነታቸው በካንሰር ሕመም ምክንያት በ88 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም ድካም ዐርፈዋል፡፡
baba shenouda
በሰሜናዊ ግብፅ፣ አስዩት ውስጥ ሐምሌ 27 ቀን 1915 ዓ.ም ሲወለዱ ናዚር ጋይድ የሚል መጠሪያ ከቤተሰባቸው የተሰጣቸው ቅዱስነታቸው፣  ቅስናን ሲቀበሉ አባ እንጦንስ ተብለው ይጠሩ የነበር ሲሆን አቡነ ሲኖዳ የተባሉት በ1955 ዓ.ም የክርስትና ትምህርት ኤጲስ ቆጶስ ተብለው በተሸሙበት ወቅት ነበር፡፡ ቅዱስነታቸው አቡነ ሲኖዳ የቅብጥ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን 117ኛ ፓትርያርክ ሆነው በወንጌላዊው ቅዱስ ማርቆስ መንበር ላይ የተሾሙት ከተአምር ሠሪው ፓትርያርክ ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቄርሎስ 6ኛ በኋላ ኅዳር 4 ቀን በ1964 ዓ.ም ነበር፡፡
ቅዱስነታቸው ከ5ኛው ክፍለ ዘመን በኋላ የቲዎሎጂ ሴሚናሪ ዲን የሆኑ የመጀመሪያው ፓትርያርክ ሲሆኑ በአገልግሎት ዘመናቸው ከ3 የአሜሪካን እንዲሁም ከ1 የጀርመን ዩኒቨርስቲ የክብር ዶክትሬት ተቀብለዋል፡፡ቅዱስነታቸው ሕይወታቸው የትሕርምት፣ የጸሎትና የአገልግሎት እንደነበር የሕይወት ታሪካቸውን የሚዘግቡ ድርሳናት የሚገልጹ ሲሆን ባለፉት 20 ዓመታት የዓለምን ሕዝብ ያስተማሩባቸው 80 መጻሕፍትን ደራሲና የቤተ ክርስቲያኗ ኦፊሴላዊ መጽሔት ኤል-ኬራዛ ዋና አዘጋጅ ነበሩ፡፡

 

በግብፅ ርዕሰ ብሔር አንዋር ሳዳት ጊዜ አክራሪ ሙስሊሞች በክርስቲያኖች ላይ የሚያደርሱት ጥቃት መጨመርና መፋፋም ያሳሰባቸው ቅዱስነታቸው በመንግሥቱ ላይ ባነሱት ተቃውሞ፣ ለ40 ወራት ከመንጋዎቻቸው ተለይተው ወደ ቅዱስ ቢሶይ ገዳም ተግዘው የአባቶቻቸውን በረከት ተካፍለው እንደነበር የሚታወቅ ሲሆን በኋለኛው መሪ ሆስኒ ሙባረክ ዘመን ወደ መንበራቸው ተመለሰው እስከ ዛሬ ድረስ ጠቦቶችን ሲጠብቁ፣ ግልገሎችና በጎችን ሲያሰማሩ ቆይተው ዐርፈዋል፡፡

 

በግብፅ ሕዝብ በተለይም በኦርቶዶክሳውያን ዘንድ ተወዳጅ አባት እንደሆኑ የሚነገርላቸው ቅዱስነታቸው በግብፃውያን ክርስቲያኖችና ሙስሊሞች መካከል ያለውን ግንኙነት ለማሻሻልና ሰላማዊ ለማድርግ ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይሉ እንደደከሙ ይመሠከርላቸዋል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሲኖዳ ኢትዮጵያን  ሁለት ጊዜ የጎበኙ ሲሆን ከመጀመሪያው ጉብኝታቸው 30 ዓመታት በኋላ በ2000 ዓ.ም ሚያዝያ ወር ላይ ያደረጉት ጉበኝት የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነበር፡፡

ጸሎታቸው ከሁላችን ጋር ይሁን፣ ማኅበራችን ማኅበረ ቅዱሳን ለግብፃዉያን ወንድም እህቶቻችንና ቅዱስነታቸውን ለሚወዱ ሁሉ መጽናናትን ይመኛል፡፡

የአብነት ትምህርት ቤት ለመደገፍ የግንባታና የቋሚ ገቢ ማስገኛ ፕሮጀክት ቀረበ

መጋቢት 7/2004 ዓ.ም.

በዳዊት ደስታ


በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የአዲስ አበባ ማእከል የማኅበራዊ አገልግሎትና ልማት ክፍል በሰሜን ሸዋ ሰላሌ ፍቼ ሀገረ ስብከት፣ በሰንዳፋ አዳማ በበኬ ደብረ ምሕረት ቅድስተ ማርያም ቤተ ክርስቲያን የሚገጥመን የአብነት ትምህርት ቤት ለመደገፍ የግንባታና የቋሚ ገቢ ማስገኛ ፕሮጀክት ዕቅድ ከባለድርሻ አካላት ጋር የካቲት 18 ቀን 2004 ዓ.ም. በደብሩ የስብከተ ወንጌል አዳራሽ ቀረበ፡፡

በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት  መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የአብነት ትምህርት ቤቶች ፕሮጀክት ክትትል ባለሙያ የሆኑት ዲ/ን ጌታዬ መኮንን የአብነት ትምህርት ቤት ነባራዊ ሁኔታን በተመለከተ ባለድርሻ አካላት ግንዛቤ እንዲኖራቸው የዳሰሳ ጥናት አቅርበዋል፡፡ በመቀጠልም ለሚተገበረው ፕሮጀክት የአዲስ አበባ ማእከል የማኅበራዊ አገልግሎትና ልማት ፕሮጀክት ን/ክፍል ጸሓፊ አቶ አንዱዓለም ተስፋዬ የፕሮጅክቱን መነሻ ሀሳብ አቅርበዋል፡፡

 

በፕሮጀክት ትግበራው የግብርና ሥራ፣ የሰብል ምርት ፕሮጀክትና የወተት ላም እርባታ ዕቅድን ጨምሮ ለአብነት ተማሪዎቹ የማደሪያና መማሪያ ክፍል፣ የመጸዳኛና ንጽህና መስጫ፣ ቤተ መጻሕፍት እና ማብሰያ የማእድ ቤት ግንባታ ያካተተ ነው፡፡ ይህን ፕሮጀክት ለመተግበር 3.8 ሚሊዮን ብር የሚፈጅ ሲሆን ከበጎ አድራጎት፣ ከማኅበራት፣ ከሠራተኛ ጉባኤያት፣ በአካባቢው ምእመናን ወጪው እንደሚሸፈን ከቀርበው ፕሮጀክት ለማወቅ ተችሏል፡፡

 

የበኬ ደብረ ምሕረት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ የሆኑት መልአከ ምሕረት ቆሞስ አባ ገብረ አማኑኤል አያኔ በበኩላቸው የአብነት ተማሪዎቹ ያለባቸውን የመጠለያ፣ የምግብ እና የአልባሳት ችግር ለመፍታት የሚተገበረው ፕሮጀክት ዐይነተኛ ሚና እንደሚኖረው እምነታቸውን ገልጸዋል፡፡

 

ለዚህ ፕሮጀክት መሳካት አጋዥ የሚሆኑ የአካባቢው ምእመናን ተገኝተዋል፡፡ ከእነዚህም መካከል ለታ ቁምቢ የተባሉ ምእመን የአብነት ተማሪዎች ላለባቸው ችግር አቅሜ በፈቀደ መጠን ለትምህርት ቤቱ መሥሪያ ለሚያስፈልገው ቁሳቁስ ለመርዳት ፈቃደኛ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡

 

በበኬ ደብረ ምሕረት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን የሚገኘውን የአብነት ት/ቤት በዘላቂነት ለመደገፍ የታቀደው ፕሮጀክት ምእመኑ እንዲያውቀው የቀረበ ሲሆን በዚህ ፕሮጀክት ዕቅድ ትግበራ ላይ ከ90 በላይ ባለድርሻ አካላት የተገኙ ሲሆን ለዕቅዱ ስኬታማነት ሁሉም የበኩሉን እንዲወጣ ጥሪ ቀርቧል፡፡

የዐቢይ ጾም ስብክት (ክፍል 5)

መጋቢት 7/2004 ዓ.ም.

በአያሌው ዘኢየሱስ

 

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

 

የዐቢይ ጾም አምስተኛ ሳምንት ሰንበት «ደብረ ዘይት» ተብሎ ይጠራል፡፡ ደብረ ዘይት ከኢየሩሳሌም በስተ ምሥራቅ የሚገኝ ተራራ ነው፡፡ ተራራው በዚህ ስም የሚጠራው ለዘይት የሚሆን የወይራ ተክል በብዛት ስለሚበቅልበት ነው፡፡ ጌታችን ቀን ሲያስተምር ውሎ በደብረ ዘይት ያድር ነበር፡፡ ለደቀ መዛሙርቱም ለሕዝቡ በምሳሌ ያስተማረውን ይተረጉምላቸው ነበር፡፡ የዓለም ፍጻሜና የዳግም ምጽአቱን ምልክት ለደቀ መዛሙርቱ ያስተማራቸው በዚሁ ተራራ ላይ ነውና የጌታን ዳግም ምጽአት የምናስብበት አምስተኛው የዐቢይ ጾም ሰንበት ስሙን ከተራራው ወስዷል ማለት ነው፡፡ ደብረ ዘይት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምዕመናን ዘንድ «እኩለ ጾም» ተብሎ ይጠራል፡፡ በዚህ ስያሜ የሚጠራውም የጾሙ ሳምንታት አጋማሽ ወይም እኩሌታ ስለሆነ ነው፡፡ አንዳንድ የቤተ ክርስቲያን አባቶች መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕለተ እሑድ፣  የደብረ ዘይት ዕለት ይመጣል ብለው ስለሚያስተምሩ በዚህ ሰንበት የሚበዙት ምዕመናን ዕለቱን በታላቅ ዝግጅት ማለትም በንስሓና በቅዱስ ቁርባን ይቀበሉታል፡፡ በዚህ ዕለት የሚሰበከው ምስባክ፣ የሚሰጠው የወንጌል ትምህርትና የሚነበቡት የሐዋርያት ሥራና የመልእክታት ንባባት በሙሉ የጌታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ሁለተኛ አመጣጥ የሚናገሩ ናቸው፡፡

ከአራቱ ወንጌላውያን (ማቴዎስ፣ ማርቆስ፣ ሉቃስ፣ ዮሐንስ) ስለ አምላካችን ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ሁለተኛ አመጣጥ እና ስለ ዕለተ ደይን ማለትም ስለ ፍርድ ቀን በስፋትና በጥልቀት የጻፈው ወንጌላዊው ቅዱስ ማቴዎስ ነው፡፡ በመሆኑም በአምሳ አንድ ቁጥሮች የተከፋፈለው ሃያ አራተኛው ምዕራፉ ሙሉ ለሙሉ የሚናገረው ስለ አስፈሪውና ስለ አስደንጋጩ የክርስቶስ ሁለተኛ አመጣጥ ነው፡፡ ምዕራፉን በሦስት ዐበይት ክፍሎች ሥር ማሰባሰብ ይቻላል፤ኢየሱስ ክርስቶስ ከመምጣቱ በፊት፣ በመጣ ጊዜ እና ከመጣ በኋላ በምድርና በሰማይ ላይ የሚከሰቱ ክስተቶች በማለት፡፡ ይሁን እንጂ በዚህ አጭር ጽሑፍ ውስጥ የሚገኙትን አምሳ አንድ ቁጥሮች ኀይለ ቃላት አድርጎ መስበክ ስለማይቻል አንዱን ቁጥር ርእስ አድርገን በመውሰድ ለመማማር እንሞክራለን፡፡

ከላይ ርእስ ተደርጎ የተወሰደው “እነዚያ ቀኖች….” የሚለው ነው፡፡ «እስከ መጨረሻ የሚጸና ግን እርሱ ይድናል፡፡» (ማቴ 24፥13) የሚለው ነው፡፡ አስቀድመን እንደ ተናገርን አምላካችን ከመምጣቱ በፊት፣ በመጣ ጊዜ እና ከመጣ በኋላ በምድርና በሰማይ የሚታዩ ታላላቅ ምልክቶች ተከስተው እስከሚያበቁ ድረስ በሰው ልጆች ዘንድ ከመቼውም ጊዜ የበለጠ ጽናት ስለሚያስፈልግ ነው መድኀኔዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ እስከ መጨረሻ የሚጸና እርሱ ይድናል በማለት በግልጥ ያስተማረው፡፡ ድንጋይ በድንጋይ ላይ ሲፈርስ፣ እኔ ክርስቶስ ነኝ ብለው የሚያውጁ አሳቾች ሲነሡና ብዙዎችን ሲያስቱ፣ ጦርንና የጦር ወሬን መስማት ተደጋጋሚ ዜና ሲሆን፣ ሕዝብ በሕዝብ ላይ መንግሥትም በመንግሥት ላይ መነሳቱ ቀላል ነገር ሲሆን፣ ረሀብ ቸነፈርና የምድር መናወጥ በተለያዩ የዓለማችን ክፍሎች ላይ ሲመጣ የሚመለከቱ የሰው ልጆች መጽናት ስለሚያስፈልጋቸው ነው እስከ መጨረሻ የሚጸና እርሱ ይድናል ተብሎ የተነገረው፡፡

ከዚህ በተጨማሪ የእግዚአብሔር ልጆች በማያምኑ ሰዎች ሲጠሉ፣ ለመከራ ተላልፈው ሲሰጡና ሲገደሉ፣ ሰዎች እርስ በእርሳቸው ተላልፈው ሲሰጣጡ፣ እርስ በእርሳቸው ሲጣሉ፣ ብዙ ሐሰተኛ ነቢያት ሲነሡና ብዙዎችን ሲያስቱ፣ ዓመጻ ሲበዛና የሰው ልጆች ፍቅር ሲቀዘቅዝ ወይም ሲጠፋ፣ ከዓለም መጀመሪያ እስከዚያ ቀንድ ድረስ ያልሆነ ከእንግዲህም ከቶ የማይሆን ታላቅ መከራ ሲሆን፣ አሳቾችና ሐሰተኞች ክርስቶሶች ለእግዚአብሔር የተመረጡትን ሰዎች እስኪያስቱ ድረስ ታላላቅ ምልክትና ድንቅ ሲያሳዩ የሚመለከቱ ሰዎች ከሃይማኖታቸውና ከእምነታቸው ሳይናወጡ እስከ መጨረሻው ድረስ በጽናት እንዲቆዩና እንዲድኑ ነው ጌታ እስከ መጨረሻ የሚቆይ እርሱ ይድናል በማለት የተናገረው፡፡

ከዚህ ሌላ የጥፋት ርኵሰት በተቀደሰችው ስፍራ (በቤተ ክርስቲያን) ቆሞ ሲታይ፣ ፀሐይ ስትጨልም፣ ጨረቃ ብርሃንዋን አልሰጥም ስትል፣ ከዋክብት ከሰማይ ሲወድቁ፣ የሰማያት ኀይላት ሲናወጡ፣ የሰው ልጅ (ኢየሱስ ክርስቶስ) ምልክት በሰማይ ሲታይ፣ የምድር ወገኖች ሁሉ ዋይ ዋይ ሲሉ፣ ወልደ እጓለመሕያው ኢየሱስ ክርስቶስ በኀይልና በብዙ ክብር መምጣቱ ሲታይ፣ መላእክቱ ከሰማያት ዳርቻ እስከ ዳርቻው ድረስ ለእርሱ የተመረጡትን ቅዱሳን ሲሰበስቡ የሚመለከትና በጽናት የሚቆይ ሰው እርሱ ይድናል ማለት ነው፡፡

ከዚህ በላይ የተመለከትናቸውና ወንጌሉ ምንም ሳያስቀር ፍንትው አድርጎ ያሳየን የዳግም ምጽአት የመጀመሪያ፣ የቀጣይና የመጨረሻ ምልክቶች በሙሉ አሳሳቢ፣ አስፈሪና አስደንጋጭ ምልክቶች ስለሆኑ እምነትና ሥራ የሌለው ሰው ካልሆነ በስተቀር ማንም ቢሆን እስከ መጨረሻው ድረስ በጽናት ሊቋቋማቸው አይችልም፡፡ በተለይም የጥፋት ርኵሰት በተቀደሰችው ቦታ ላይ ሲቆም፣ አሳቾች ለእግዚአብሔር የተመረጡትን ሰዎች እስከሚያስቱ ድረስ ታላላቅ ምልክትና ድንቅ ሲያሳዩ መመልከትና ፀሐይ፣ ጨረቃ፣ ከዋክብትና የሰማያት ኀይላት  ብርሃናቸውን ሲነፍጉ፣ ከሰማይ ሲረግፉና ሲናወጡ መስማትና ማየት በሃይማኖትና በምግባር የማይኖረውን ሰው ሊያጸናው አይችልም፡፡ ዛሬ በተቀደሰችው ቦታ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የጥፋት ርኵሰት መቆሙን የሚያመለክቱ ብዙ ምልክቶች በገሃድ እየታዩ ነው፤ከሊቅ እስከ ደቂቅ በጥፋትና በርኵሰት ሥራ እንጂ በእምነትና በጽድቅ ሥራ ላይ ወይም ኢየሱስ ክርስቶስን ለመቀበል በሚያስችሉ ሥራዎች ላይ ሲተጋ አይታይምና፡፡ በመሆኑም አምና እና ዘንድሮ አሳቾች መናፍቃን የክርስቶስ ነን ወይም ክርስቶስ ከእኛ ጋር ነው እያሉ ብዙዎችን ሲያስቱ፣ መንግሥት በመንግስት ላይ ሕዝብም በሕዝብ ላይ ሲነሣ፣ በዓለማችን የተለያዩ ቦታዎች ላይ ምድር ስትናወጥ፣ ረሀብና ቸነፈር ሲሠለጥኑ እየተመለከተ ያለ ሰው በዚሁ ምክንያት በሃይማኖቱ ሊጸና ስላልቻለ የምጥ ጣር መጀመሪያ በተባሉት በእነዚህ ምልክቶች ሲፈናቀል እየታየ ነው፡፡

እንዲህ ዓይነቱ ሰው ከኢየሱስ ክርስቶስ መምጣት በፊት በሚታዩት እነዚህ የምጥ ጣር መጀመሪያዎች ወይም የመጀመሪያ ምልክቶች መታየት ሃይማኖቱን የሚለውጥ ከሆነ የጥፋት ርኩሰት በቤተ ክርስቲያኑ ዓውደ ምሕረት ላይ ቆሞ ስለ ጥፋት ሲሰብክ ሲመለከት እንዴት ነው ሊጸና የሚችለው? እነዚህን ምልክቶች የተለመዱ የሰዎችና የተፈጥሮ አደጋዎች ናቸው ብሎ የሚያምንና በዚያ ዙሪያ መፍትሔ ለመስጠት የሚራወጥ ሰው ይህ ሊሆን ግድ ነውና ከጥፋት ተጠበቁ እንዲሁም ዳሩ ግን መጨረሻው ገና ነው የሚለውን አምላካዊ ቃል በጽናት ሊያምንና ሊተገብር የሚችለውስ እንዴት ነው? ዲያቆን እገሌ ወይም ቄስ እገሌ ወይም አባ እገሌ ሰው በመሆናቸውና ደካማ የሆነውን ሥጋ በመልበሳቸው የሚፈጽሙአቸውን ስሕተቶች ሲመለከት ሃይማኖቱን ረግሞ ከመናፍቃን ጋር ጽዋውን ሊያነሣ የሚጣደፈው ሰው ነገ ያሳሳቱት አሳቾች የተመረጡትን ሰዎች እስከ ማሳሳት ሲደርሱ ሲመለከት እንዴት አድርጎ ነው ሊጸና የሚችለው? እዚህ ላይ ንባባችሁን ጥቂት በማቆም በተመስጦ ውስጥ ሁኑ እና ራሳችሁን በክርስቶስ ቃል እንዲህ ብላችሁ ጠይቁት፡- «ነገር ግን የሰው ልጅ በመጣ ጊዜ በምድር እምነትን ያገኝ ይሆንን?» ሉቃ 18፥8፡፡

ይህ ቃል አስፈሪ ቃል ነው! ይህ ቃል ውስጣችንን የሚመረምር ቃል ነው! ይህ ቃል ማንነታችንን የሚያሳይ ቃል ነው! ይህ ቃል ማንነታችንን የሚገልጥ ቃል ነው! ይህ ቃል እምነትና ጽናት በእኛ ዘንድ እንደሌለ የሚመሰክር ቃል ነው! ይህ ቃል ባዶ መሆናችንን የሚያሳውቅ ቃል ነው! ይህ ቃል እውነት ነው! ይህ ቃል የእውነት አምላክ የኢየሱስ ክርስቶስ ቃል ነው! ዛሬ እምነት ከሰው ልጆች ዘንድ እየመነመነ ነው፡፡ በእምነት የሚፈጸሙ ተግባራት እየጠፉ ነው፡፡ እምነት ስለሌለም ጽናት እየጠፋ ነው፡፡ ጽናት  ስለሌለም ሰው ሁሉ እየጠፋ ነው፡፡ «እምነትን ያገኝ ይሆንን?» የሚለው ቃል «ያገኛል» ማለት አይደለም፤«አያገኝም» ማለት ነው እንጂ፡፡ «በመጣ ጊዜ» የሚለው ቃልም ለሁለተኛ ጊዜ ለፍርድ ሲገለጥ ወይም በዳግም ምጽአቱ ሲገለጥ ማለት ነው፡፡ የሚመጣውም እስከ መጨረሻው ድረስ በእምነትና በጽናት በመቆየት መንግሥቱን ሊያወርሰን የሚፈልገው መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ሰዎች እምነትና ሥራን አስተባብረው ካልያዙ ግን መንግሥቱን አያወርሳቸውም፡፡ በሰዎች ዘንድ በእምነትና በሥራ የሚገለጥ ጽናት ከሌለም መንግሥቱን ሊወርሱ አይችሉም፡፡ እምነት ብቻ አያድንም! ሥራ ብቻ አያድንም! በባዶ ነገር ላይ መጽናትም አያድንም! እምነትንና ሥራን አስተባብሮ በመያዝ በእነዚህ በሁለቱ ላይ መጽናት ግን ያድናል!! ሰው እምነትና ሥራን አስተባብሬ ይዤአለሁ እያለ በእነዚህ ላይ ሊጸና ካልቻለና በትንሹም ሆነ በትልቁ ምክንያት ወይም ፈተና የሚወድቅ ከሆነም አይድንም፡፡

ከመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ እስከ መጨረሻው ድረስ ሊጸኑ የቻሉና ያልቻሉ ብዛት ያላቸው ሰዎችን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ለምሳሌ፡- ጻድቁ ኢዮብ፣ ነቢዩ ኤልሳዕና ሐዋርያት ለጽናት ልዩና ድንቅ ምሳሌዎቻችን ናቸው፡፡ ጻድቁ ኢዮብ ቤቱን፣ ንብረቱን፣ ከብቶቹንና አሥር ልጆቹን በአንድ ቀን ውስጥ ያጣ ሰው ነበር፡፡ ይህ ሳይበቃውም መላው ሰውነቱ በከባድ ቁስል ተመትቶ ከፍተኛ መከራና ሥቃይ ውስጥ ገብቶ ነበር፡፡ ይህን ሁሉ ፈተና ያመጣበት ሰይጣን ሲሆን ምክንያቱም እርሱን በእግዚአብሔር ላይ ያለውን እምነት በሥራና በጽናት መግለጽ አይችልም በማለት ተስፋ ስላደረገ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ የኢዮብ አሳብና የሰይጣን አሳብ፤የኢዮብ እምነትና የሰይጣን እምነት፣ የኢዮብ ሥራና የሰይጣን ሥራ፣ የኢዮብ ጽናትና የሰይጣን ጽናት አንድ ሊሆን ስላልቻለ ኢዮብ ሰይጣንን በአራቱም ውጊያዎች ፈጽሞ አሸንፎታል፡፡ በአሳብ፣ በእምነት፣ በሥራና በጽናት፡፡

እንደ ሰው ሰውኛው (እንደ እኛ) አስተሳሰብ ኢዮብን የገጠሙት ፈተናዎች በእምነቱና በሥራው እስከ መጨረሻው ድረስ ሊያጸኑት የሚችሉ አልነበሩም፡፡ እኛ ያሉኑን ነገሮች ማለትም ሀብታችንን፣ ንብረታችንን፣ ልጆችንንና ጤናችንን አጥተን አይደለም እነዚህ ሁሉ ተሟልተውልን እግዚአብሔርን ልናምነው፣ እርሱን ደስ የሚያሰኙትን የጽድቅ ሥራዎች ልንሠራና በእነዚህ ላይ ልንጸና አልቻልንም፡፡ ሁሉንም ነገር ሰጥቶን እኮ ነው የለህም የምንለው! ሰዎች ያላቸውን ሳያጡ እኮ ነው እርሱን የሚክዱት! ሰዎች ራሳቸውን ወይም ሆዳቸውን ጥቂት ካመማቸው እኮ ነው እግዚአብሔርን የለህም ለማለት የማይሰንፉት! ኢዮብ ግን አሥር ልጆቹን ጨምሮ ሁሉንም ነገር ቢያጣና እርሱ ራሱ የቆሰለ ገላውን በገል እስከ መፋቅ ቢደርስም እንዲህ ነበር ያለው፡- «. . . እግዚአብሔር ሰጠ እግዚአብሔርም ነሣ፤የእግዚአብሔር ስም የተመሰገነ ይሁን፡፡» ኢዮ 1፥21፡፡

ያለ ነገርን ሙሉ ለሙሉ አጥቶ እግዚአብሔርን ማመስገን መቻል በእምነትና በሥራ ላይ የተመሠረተ ጽናት ነው፡፡ የቆሰለ አካልን ከእግር ጥፍር እስከ ራስ ጠጉር ድረስ በገል እየፋቁ የእግዚአብሔርን ስም ለማመስገን መነሣት በእምነትና በሥራ ላይ የተመሠረተ ጽናት ነው፡፡ እስከ መጨረሻ ድረስ በእምነት መጽናት ደግሞ ድኅነትን ስለሚያሰጥ ጻድቁ ኢዮብ ከልጆቹ ቁጥር በስተቀር የነበሩት ነገሮች ሁለት እጥፍ ሆነው ተመልሰውለታል፤የልጅ ልጆቹንም እስከ አራት ትውልድ ድረስ ሊያይ ችሏል፣ ሸምግሎና ዕድሜ ጠግቦም ሞቷል፡፡ የሚጸና ሰው ዋጋ እጥፍ ነው፡፡ የሚያዳክሙና ከእግዚአብሔር ሊለዩ የሚሞክሩ ሚስቶችን እንደ ጻድቁ ኢዮብ «አንቺ ከሰነፎቹ ሴቶች እንደ አንዲቱ ተናገርሽ፤ ከእግዚአብሔር እጅ መልካሙን ተቀበልን፤ክፉ ነገርንስ አንቀበልምን?»  (ኢዮ 2፥10) ማለት እምነት ነው! ሥራ ነው! ጽናትም ነው! በእምነትና በጽናት ላይ የሚመጡ ባልንጀራዎችን “የምታዳክሙ ባልንጀራዎች” ማለትም ጽናት ነው!

ኤልሳዕ መምህሩ ኤልያስ ከእርሱ ተለይቶ በእሳት ሰረገላና ፈረሶች ወደ ሰማይ ከማረጉ በፊት ከቤቴል እስከ ዮርዳኖስ ማዶ ድረስ በሚገኙት አራት ከተሞች ውስጥ የሚኖሩ የነቢያት ልጆች «እግዚአብሔር ጌታህን ከራስህ ላይ እንዲወስደው አውቀሃልን?» (2ኛ ነገ 2፥3እና5) በማለት ጽናቱን አናውጠው ከጌታው ከኤልያስ ሊለዩትና በመጨረሻ ሊያገኘው የነበረውን እጥፍ መንፈስ ሊስቀሩበት ሞክረው ነበር፡፡ ኤልሳዕ ግን ጽናቱን «አዎን አውቄአለሁ፤ዝም በሉ፤. . .» (2ኛ ነገ 2፥3እና5) በማለት አረጋግጦላቸዋል፡፡ ከቤቱ ወጥቶ እግዚአብሔር ወደሚመለክበት ሥፍራ በመሔድ ላይ ያለ ወጣትን ባልንጀሮቹ ዛሬ እኮ «አርሴ» እና «ማንቼ» ግጥሚያ እንዳላቸው አላወቅህምን? ሲሉት «አዎን አውቄአለሁ፤ዝም በሉ» በማለት ከእግዚአብሔር ጋር ያለውን ግንኙነት በእምነቱና በሥራው ላይ እስከ መጨረሻ ድረስ በመጽናት መንገዱን የማይቀጥል ከሆነ እምነቱን በሥራና በጽናት አልገለጠምና በፍርድ ቀን የጌታውን መንግሥት ሊወርስ አይችልም፡፡ ይህን የምለው የነጮቹን ኳስ ግጥሚያ ለማየት ሲሉ የተሰጣቸውን የስብከት ወይም የሰዓታት ወይም የማኅሌት አገልግሎት ሰርዘው ወደዚያው የሔዱ ሰዎችን ስለማውቅ ወይም ራሳቸው ስለ ነገሩኝ ነው፡፡ እንብላ፣ እንጠጣ፣ እንቃም፣ እናጭስ፣ እንጨፍር፣ እንሴስን. . . ወዘተ የሚሉትንም በጽናት «ዝም በሉ!» በማለት አልፎ መምጣት እስከ መጨረሻው ድረስ መጽናት ካልተቻለ የሰዎች ውድቀት የከፋ ነው የሚሆነው፡፡

የሐዋርያት ጽናትም ከዚህ ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ እነርሱ ሁሉንም ነገር ትተው መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በጽናት ከተከተሉት በኋላ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ እንደ አረጋዊነቱ እነርሱን በመወከል «እነሆ እኛ ሁሉን ትተን ተከተልንህ፤ እንኪያስ ምን እናገኝ ይሆን?» (ማቴ 19፥27) የሚል መሠረታዊ ጥያቄ ለጌታ አቅርቦለት ነበር፡፡ አምላካችንም ለቅዱስ ጴጥሮስ ብቻ ሳይሆን እርሱ ለወከላቸው ለአሥራ ሁለቱ ሐዋርያት እንዲህ የሚል መልስ ሰጥቶአቸዋል፡- «እውነት እላችኋለሁ፡- እናንተስ የተከተላችሁኝ በዳግመኛ ልደት የሰው ልጅ በክብሩ ዙፋን በሚቀመጥበት ጊዜ እናንተ ደግሞ በአሥራ ሁለቱ የእስራኤል ነገድ ስትፈርዱ በአሥራ ሁለት ዙፋን ትቀመጣላችሁ፡፡» ማቴ. 19፥28፡፡ ጌታ ይህን ከነገራቸው በኋላ ያለውን ሁሉ የተወ ሰው እንደ ኢዮብና እንደ ኤልሳዕ ሁለት እጥፍ ዋጋ እንደሚቀበሉ እንዲህ በማለት አስረግጦ ነግሮአቸዋል፡- «. . . የተወ ሁሉ መቶ እጥፍ ይቀበላል፤የዘላለምንም ሕይወት ይወርሳል፡፡» ማቴ.19፥29፡፡

አስቀድመን እንደ ተናገርን የሚጸና ሰው ዋጋ እጥፍ ድርብ ወይም መቶ እጥፍ ነው፡፡ በክርስትና ሳይተዉ መቀበል አይቻልም፡፡ ዛሬ ብዙዎች ያላቸውን ሀብት፣ ቤት፣ ንብረት፣ ልጆች. . . ወዘተ ሊተዉ አልቻሉም፡፡ ይህ በእግዚአብሔር ፈቃድ ለዚህ አገልግሎት ለተመረጡ አባቶች ብቻ ስለሆነና ሁሉም ያለውን ትቶ በምንኩስና ሕይወት እርሱን እንዲከተሉት ስላልፈቀደ ሁሉም መነኩሴ ወይም መነኩሲት ሊሆን አይችልም፤በግድ ልሁን ቢልም አይሳካለትም፡፡ ይሁን እንጂ እግዚአብሔር አምላክ ሰዎች ሁሉ አጥብቀው እንዲተዉለት የሚፈልገው ነገር አለ፤እርሱም ኀጢአት ነው፡፡ ዛሬ ብዙዎችን እስከ መጨረሻው ድረስ እንዲጸኑ፣ እንዲድኑና ዘላለማዊ ሕይወት እንዲወርሱ የማያደርጋቸው ኀጢአት ነው፡፡ አንድ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አባል ወደ ክርስትና እምነት የተጠራው እስከ ሞት ድረስ በመጽናት የዘላለም ሕይወት ለመውረስ ስለሆነ ከኀጢአት መሸሽ እንጂ ኀጢአትን መከተል አልተፈቀደለትም፡፡ «እስከ ሞት ድረስ የታመንህ ሁን፤የሕይወትንም አክሊል እሰጥሃለሁ፡፡» (ራእ 2፥10) በማለት የተናገረው እኮ የእግዚአብሔር አብ እና የድንግል ማርያም ልጅ ጌታችን፣ አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ጽናትና መታመን ከኀጢአትና ከጥፋት ጋር ሊስማሙ አይችሉም፡፡ ኀጢአት እስከ ሞት ድረስ የታመንን እንድንሆን አያደርገንም፡፡

ኢዮብ፣ ኤልሳዕና ሐዋርያት በእምነት፣ በሥራና በጽናት የሕይወትን አክሊል ተቀብለዋል፡፡ ሶምሶን፣ ግያዝና ዴማስ ግን እስከ መጨረሻ ድረስ ሊጸኑ ስላልቻሉ ሊጸድቁ አልቻሉም፡፡ በአንድ ወቅት ታላላቅ መንፈሳዊ አባቶች ተብለው የተጠሩ እነዚህ ሰዎች በፈተና ሊጸኑ ስላልቻሉ ለሌሎች ሁለት እጥፍ ሆኖ የተሰጠውን ዋጋ ሊቀበሉ አልቻሉም፤ አልተባረኩምም፡፡ መጽሐፍ ጽናት ስለሚያሰጠው በረከት ሲናገር እንዲህ ብሏል፡- «በፈተና የሚጸና ሰው የተባረከ ነው፡፡» ያዕ 1፥12፡፡ ለመባረክም መጽናት ያስፈልጋል ማለት ነው፡፡ በፍርድ ቀን «ኑ፤ዓለም ከተፈጠረበት ጊዜ ጊዜ ጀምሮ የተዘጋጀላችሁን መንግሥት ውረሱ፡፡» (ማቴ 25፥34) የሚለውን የእግዚአብሔር ቡራኬ ለመቀበል እስከዚያው ቀን ድረስ በእምነትና በሥራ በጽናት መቆየት ያስፈልጋል፤ማስፈለግ ብቻ ሳይሆን ግድ ነው!!

ስለሆነም ዛሬ በዐቢይ ጾም አምስተኛ ሰንበት ላይ ሆነን የደብረ ዘይትን በዓል ስናከብር እስከ ጌታችን ዳግም ምጽአት ድረስ በእምነት፣ በሥራና በጽናት እንድንቆይ እርሱን «አንተ አድነን!» ልንለው ይገባናል፡፡ እንደ ጸኑት ሁለት እጥፍ ዋጋ እንዳናገኝ ዓለም በአናንያ፣ በአዛርያና በሚሳኤል ዙሪያ ያነደደችውን የፈተና እሳት በእኛም ሕይወት ዙሪያ አንድዳለችና በእሳቱ ከመሟሟቅ ይልቅ እሳቱን የምናጠፋበትን የእምነት ጽናት እንዲያድለን እንጠይቀው፡፡ ዛሬ በእምነትና በእምነት ሥራ የምናየውና የምንሰማው ዜና ሁሉ ተስፋ የሚያስቆርጥ እንጂ የሚያጸና ስላልሆነ እግዚአብሔር አምላክ ተስፋችንን እንዲሁም ጽናታችንን እንዲያለመልመልን እንጠይቀው፡፡ የሰዎች ዐይኖች በእግዚአብሔር ሥራዎች ላይ ከማተኮር ይልቅ በዲያብሎስ ሥራዎች ላይ እጅግ አተኩረዋልና ዐይኖቻቸውን ከዚህ ክፉ ሥራ መልስ እንበለው፡፡

የደብረ ዘይት በዓል የዝግጅት በዓል ነው፡፡ የደብረ ዘይት ከእግዚአብሔር ጋር የምንሆንበትን ቀን የምንናፍቅበት በዓል ነው፡፡ የደብረ ዘይት በዓል ከእግዚአብሔር ጋር አንድ የምንሆንበት በዓል ነው፡፡ ዳግም ምጽአት ከእግዚአብሔር ዋጋ የምንቀበልበት ቀን ነው፡፡ ዳግም ምጽአት ከእግዚአብሔር በስተ ቀኝ የምንቆምበት ቀን ነው፡፡ ዳግም ምጽአት ዐይን ያላየውን፣ ጆሮ ያልሰማውንና በልቦናም ያልታሰበውን የእግዚአብሔር መንግሥት ለመውረስ የምንሸጋገርበት ቀን ነው፡፡ ስለሆነም ቀኑን በፍጹም እምነት ከልባችን ሆነን በመጾም፣ በመጸለይ፣ በመስገድና በመመጽወት እናንክብረው እንጂ ከአዲስ አበባ ወደ ደብረ ዘይት ወጣ ብለን ለመዝናናት፣ ያገኘነውን ለመብላትና ለመጠጣት እንዲሁም ከዕለቱ በዓል ጋር የማይገናኙ ተራ ወሬዎችን ለማውራት እንዳናደርገው እንጠንቀቅ!! የአምላካችን የእግዚአብሔር ፍቅር፣ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ እና የመንፈስ ቅዱስ ኅብረት ከእኛ ጋር ይሁን፤አሜን፡፡

ይቆየን፡፡

በጎውን ሁሉ ለእኛ ያደረገና የሚያደርግ እግዚአብሔር ስሙ የተመሰገነ ይሁን፤አሜን፡፡

CALL FOR PAPER copy

የጥናታዊ ጽሑፍ ግብዣ

CALL FOR PAPER copy

CALL FOR PAPER

የአሰቦት ገዳም ደን ዳግም ቃጠሎ

መጋቢት 3/2004 ዓ.ም
በእንዳለ ደምስስ
የአሰቦት ገዳም ደን ዳግም በመቃጠል ላይ ይገኛል፡፡ ከመጋቢት 2/2004 ዓ.ም.ከቀኑ አሥር ሠዐት ጀምሮ መነሻው ባልታወቀ ምክንያት ቃጠሎው በአዲስ መልክ እንደተቀሰቀሰ የገዳሙ ማኅበረ መነኮሳት ገልጸዋል፡፡

ከገዳሙ መነኮሳት በደረሰን የድረሱልን ጥሪ መሰረት እሳቱን ለማጥፋት ከአቅማቸው በላይ እንደሆነ በመግለጽ የሚመለከተው አካል አስቸኳይ መፍትሔ እንዲፈልግላቸው በመማጸን ላይ ይገኛሉ፡፡ ከቀኑ አሥር ሠዐት የጀመረው ቃጠሎ በአባ ሳሙኤል ገዳም አቅጣጫ ሲሆን ከፍተኛ የደን ሀብት የያዘና ብዛት ያላቸው የዱር እንስሳትና አእዋፍ የሚገኙበት ነው፡፡ እንዲሁም ራሣቸውን ለእግዚአብሔር አሳልፈው የሰጡ መናንያን ስለ ሀገርና ወገን  ዘግተው የሚጸልዩበት ቦታ እንደሆነ መነኮሳቱ ያስረዳሉ፡፡ ይህንን የደን ሀብት ከቃጠሎው ለመታደግ ለሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት፤ ለወረዳ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት፤ ለፖሊስና ለፌደራል ፖሊስና ለምእመናን የድረሱልን ጥሪ በማሰማት አሳቱን ለማጥፋት የሚችሉትን ሁሉ በማድረግ ላይ እንደሚገኙ ገልጸዋል፡፡ ሆኖም ቃጠሎውን በቁጥጥር ሥር ለማድረግ እንዳልተቻላቸውና ወደ አባ ሳሙኤል ገዳም በመገስገስ በ100 /አንድ መቶ/ ሜትር ርቀት ላይ እንደደረሰ የገዳሙ መጋቢና ም/አበምኔት አባ ዘወልደ ማርያም በሀዘን ገልጸዋል፡፡ የቃጠሎው መባባስ ስጋት ውስጥ የከተታቸው መሆኑንና በዚሁ የሚቀጥል ከሆነ ጽላቱን ለማውጣት እንደሚገደዱ በመግለጽ  የድረሱልን ጥሪያቸውን በማሰማት ላይ ናቸው፡፡

የገዳሙ አበምኔት አባ ተክለ ማርያም በአሁኑ ወቅት ለመንገዱ ሥራና በደኑ ቃጠሎ ዙሪያ መፍትሔ እንዲፈለግለት በተለይም መንግስት ጥበቃ እንዲመድብ አቤቱታ ለማቅረብ አዲስ አበባ ይገኛሉ፡፡ ከቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ ጋር በጉዳዩ ዙሪያ ውይይት ማድረጋቸውን የገለጹት አበምኔቱ ለክቡር ጠቅላይ ሚኒስቴር መለስ ዜናዊ እንደሚያሳውቁና በጥበቃ ዙሪያ ያለውን ችግር በአጭር ጊዜ ውስጥ እንደሚፈታ ቅዱስነታቸው ቃል ገብተውልናል ብለዋል፡፡

የአሰቦት ገዳም ደን ከየካቲት 20 እስከ የካቲት 24/2004 ዓ.ም. ድረስ ሲቃጠል ቆይቶ በመነኮሳቱ፤ በፌደራል ፖሊስ፤ በኦሮሚያ ፖሊስና ምእመናን ከፍተኛ ተጋድሎ መጥፋቱ የታወሳል፡፡ አንድ ሳምንት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ዳግም ቃጠሎው መቀስቀሱ እጅግ አሳሳቢ አድርጎታል፡፡