ቀዳም ሥዑር

ሚያዝያ 6፣2004 ዓ.ም.

ቅዳሜ፡

ቀዳም ሥዑር ይባላል፡፡ በዚች ዕለች ከድሮው በተለየ መልኩ የጌታችንን መከራ በማሰብ በጾም ታስባ ስለምትውል የተሻረችው ቅዳሜ ትባላለች፡፡

የማትጾመዋ ቅዳሜ ስለምትጾም ስዑር /የተሻረች/ ተብላለች በዓል መሻርን አይመለከትም በቀዳም ሥዑር  ሌሊት ሥርዓቱ የሚጀመረው በመኀልየ ሰሎሞን ምንባብ ነው፡፡ ማኀሌቱም እዝሉ እየተቃኘ እየተመጠነ፣ እየተዘመመ እየተመረገደ እየተጸፋ ያድራል፡፡ ጥዋት አቡን መዋሥዕት ውዳሴ ማርያም ዜማ ተደርሶ ወለመልአከ ሕይወትሰ ሰቀልዎ በሚለው ሰላም ይጠናቀቃል፡፡በዚህ ዕለት ልብሰ ተክህኖ የለበሱ ካህናትና ዲያቆናት ቄጤማ ተሸክመው ቃጭል ሲያቃጨሉ መታየታቸው ዕለተ ትንሣኤውን ለሚናፍቅ ምእመን ትልቅ ብስራት ነው፡፡

 

ለምለም ቅዳሜ፡- ካህናቱ ለምእመናን ለምለም ቀጤማ የሚያድሉበት ዕለት ስለሆነ በዚህ ተሰይሟል፡፡ ቀጤማውንም ምእመናን እስከ ትንሣኤ ሌሊት በራሳቸው ላይ ያስሩታል፡፡

በቀዳም ስዑር ቀሳውስቱና ዲያቆናቱ ቃጭል /ቃለዓዋዲ/ እየመቱ ገብረ ሰላመ በመስቀሉ ትንሣኤሁ አግሃደ የሚለውን ያሬዳዊ ዜማ በመዘመር፤ ጌታ በመስቀሉ ሰላምን እንደሰጠን እና ትንሣኤውንም እንደገለጠልን በማብሰር፤ ቄጤማውን ለምእመናን ይሰጣሉ፡፡ ምእመናኑም በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የሚውል ገጸ በረከት ያቀርባሉ፡፡ ቄጤማውንም በራሳቸው ያስራሉ፡፡ ይህም አይሁድ ጌታችንን እያሰቃዩ ሊሰቅሉት ባሉ ጊዜ የእሾህ አክሊል ጭንቅላቱ ላይ ያሠሩበትን ድርጊት የሚያስታውስ ነው፡፡  

የቀጤማው አመጣጥና ምስጢርም ከአባታችን ከኖኅ ታሪክ ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ምድር በማየ አይኅ /በጥፋት ውኃ/ በጠፋችበት ወቅት የኖኅ ታማኝ መልእክተኛ ርግብ የውኃውን መጉደል ያበሰረችው ቀጤማ ይዛ በመግባት ነው፡፡

ዛሬም ለሐዲስ ኪዳን ክርስቲያኖች የኃጢአት ውኃ ጐደለ፣ የኃጢአት ውኃ ጠፋ በክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ነጻነት ተሰበከ ታወጀ በማለት ካህናት ቄጠማ ይዘው ምእመናንን ያበሥሩበታል፡፡

ቅዱስ ቅዳሜ ይባላል፡፡ ቅዱስ ቅዳሜ መባሉ ቅዱስ የሆነ እግዚአብሔር በጥንተ ተፈጥሮ ፍጥረታትን አከናውኖ ከፈጠረ በኋላ በዚህ ቀን ከሥራው ሁሉ ያረፈበት ነው፡፡ በዘመነ ሐዲስ ደግሞ የማዳን ሥራውን ሁሉ ፈጽሞ በሥጋው በመቃብር ሲያርፍ፣ በነፍሱ ሲዖልን በርብሮ ባዶዋን አስቀርቷታል፡፡ በዚያ ለነበሩት ነፍሳትም የዘለዓለም ዕረፍትን ያወረሰበት ዕለት ስለሆነ ከሌሎቹ ዕለታት የተለየ ዕለት ለማለት ቅዱስ ቅዳሜ ተብሏል፡፡

ምእመናን ሆይ፣ በአጠቃላይ ሥርዓተ ሕማሙን፤ ሰሙነ ሕማማት ብለው የተለየ ሥርዓት አውጥተው አባቶቻችን ተግተው ያቆዩልንን ሥርዓተ መላእክት ልንጠብቀውም ልንጠቀምበት ይገባል፡፡ የዕለታቱን ክብርና ስያሜ ከማወቅና ከመረዳት ጋር በዕለታቱ የታዘዙትን ሃየማኖታዊ ግዴታዎችን መወጣት ከሁላችንም ይጠበቃል፡፡

ምንጭ፡- ስምዐ ተዋሕዶ የስምዐ ጽድቅ ልዩ እትም ዘሰሙነ ሕማማት፣ ማኅበረ ቅዱሳን፣ ሚያዝያ 2004፣ አዲስ አበባ፡፡

ejig yetekeberu_yealemloriet

እጅግ የተከበሩ የዓለም ሎሬት ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ አረፉ

ሚያዝያ 04፣ 2004ዓ.ም

እንዳል ደምስ

ejig yetekeberu_yealemlorietእጅግ የተከበሩ የዓለም ሎሬት ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ ባደረባቸው ሕመም ምክንያት በህክምና ሲረዱ ቆይተው በተወለዱ በ80 ዓመታቸው ሚያዚያ 2/2004 ዓ.ም. ምሽት ላይ ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል፡፡ እጅግ የተከበሩ የዓለም ሎሬት አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ ከአባታቸው ከአቶ ተክሌ ማሞ እና ከእናታቸው ከወ/ሮ ፈለቀች የማታወርቅ በጥቅምት ወር 1924 ዓ.ም. በአንኮበር ከተማ ተወልደዋል፡፡ የአንደኛ ደረጃ ትምህርታቸውን በአዲስ አበባ፣ እንዲሁም የከፍተኛ ትምህርታቸውን በእንግሊዝ አገር በሚገኘው የሥነ ጥበብ አካዳሚ በሥነ ስዕል በቅርፃ ቅርጽና በሥነ ሕንፃ ዲዛይን ተከታትለዋል፡፡

በነበራቸው የሥነ ስዕል ዝንባሌ ታላላቅ ሥራዎችን የሠሩ ሲሆን በወጣትነት ዘመናቸው በ1957 ዓ.ም. ከክቡር ዶክተር ከበደ ሚካኤል ጋር በኢትዮጵያው ንጉሠ ነገሥት ቀዳማዊ ኃ/ሥላሴ እጅ የመጀመሪያውን የኢትዮጵያ የሥነ ጥበብ ተሸላሚ ለመሆን ችለዋል፡፡ ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ የአራት ዓለም አቀፍ አካዳሚዎች አባል ሲሆኑ በተሰማሩበት የሥነ ሥዕል ጥበብ በዓለም ላይ ከፍተኛ ሚና ለተጫወቱ ታላላቅ ሰዎች የሚሰጠውን የዓለም ሎሬት የተሰኘውን ማዕረግ አግኝተዋል፡፡ እስካሁን ድረስም ከዘጠና ሰባት በላይ የዓለም አቀፍ ሽልማቶችን ከተለያዩ ተቋማት አግኝተዋል፡፡

ጊዜ የማይሽራቸው ታላላቅ የሥዕል ሥራዎች ለዓለም ያበረከቱ ሲሆን በስዕሎቻቸውም ሥርዓተ አምልኮን፣ ማኅበራዊ አኗኗር የማኅበረሰቡን ደስታና ሃዘንና ጀግንነቱን ሥልጣኔውና ሀገር ወዳድነትን የሚያንጸባርቁ ሥራዎችን አበርክተዋል፡፡ በተለይም ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ካላቸው ጥልቅ ፍቅርና እምነት በመነጨ ለተለያዩ ቤተ ክርስቲያናት እንዲሁም በስቱዲዮአቸውና በጸሎት ቤታቸው የሚገኙ መንፈሳዊ ስዕላትን አበርክተዋል፡፡ ከሠሯቸው መካከልም በገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን የሚገኙ በግድግዳ ላይ የተሠሩ መንፈሳዊ ስዕላትን በቀለም ቅብ፣ በባለቀለም ጠጠሮች፣ በክርክም መስታወቶችና በሞዛይክ ከታወቁትና ስመ ጥር ከሆኑት ሰዓሊ ብላታ እምአዕላፍ ኅሩይ ጋር ሠርተዋል፡፡ በተለያዩ ዓለም አቀፍ ሙዚየሞች ውስጥም ስዕሎታቸው በክብር ተቀምጠውላቸው በጎብኚዎች እየታዩ ይገኛሉ፡፡ ኢትዮጵያን በማስተዋወቅ ረገድም በስዕሎታቸውና በቅርፃቅርጾቻቸው አማካይነት ከፍተኛ ሚና የነበራቸው ሲሆን “ቪላ አልፋ” የተሰኘው ባለ 22 ክፍሎች መኖሪያ ቤታቸውና የግል ስቱዲዮአቸው ውስጥ ይህንኑ ለማንጸባረቅ ጥረት አድርገዋል፡፡

በቪላ አልፋ ስቱዲዮ ውስጥ የአክሱም ሐውልት፣ የጎንደር ፋሲለደስ፣ የሐረር ግንብ፣ የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት፣ ቅዱሳት ስዕላት፣ የተወለዱበት አንኮበር የሚገኘው ቤተ መንግሥት የሚያስደንቁ ባህላዊ፣ ታሪካዊ፣ ሃይማኖታዊና ሀገራዊ እሴቶችን አካቶ የያዘ ነው፡፡

በንግግራቸው ስመ እግዚአብሔርን መጥራት የሚያዘወትሩት እጅግ የተከበሩ የዓለም ሎሬት አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ በዋናው መግቢያ በራቸው ላይ “የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው” የሚል ጥቅስ በትልቁ ጽፈዋል፡፡ “እንደማንኛውም ዓይነት የጥበብ ሥራ በሠራሁ ጊዜ እኔ በጥበቤ ታላቅ ነኝ የሚል ትምክህት እንዳይቀርበኝ ዘወትር እንዳነበው ነው የጻፍሁት” በማለት ከዚህ በፊት በማኅበረ ቅዱሳን ለሚታተመው ሐመር መጽሔት ጋዜጠኞች መግለጻቸው ይታወሳል፡፡

በዓለማችን ላይ ከሚገኙ ስመጥርና ታላላቅ ከተሰኙ 200 ሰዎች ጋር የሕይወት ታሪካቸውንና የኢትዮጵያ ባንዲራ በጨረቃ ላይ እንዲያርፍ የተደረገ ሲሆን በደረሰባቸው የጨጓራ አልሰር ህመም ምክንያት በህክምና ሲረዱ ቆይተው በተወለዱ በ80 ዓመታቸው ማክሰኞ ምሽት ይህችን ዓለም ተሰናብተዋል፡፡ ሥርዓተ ቀብራቸው ሚያዚያ 6/2004 ዓ.ም. ቅዳሜ በቅድሥት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ይፈጸማል፡፡

ዝግጅት ክፍላችን ለመላው ቤተሰቦቻቸው ወዳጅ ዘመዶቻቸውና አድናቂዎቻቸው መጽናናትን ይመኛል፡፡

ከጲላጦስ አደባባይ እስከ ሊቶስጥራ

{gallery count=1 width=350 height=300 counter=1 links=0 alignment=center animation=3000}Sekelete2{/gallery}

ማኅበረ ቅዱሳን የሥራ አመራር ጠቅላላ ስብሰባውን አካሔደ፡፡

02/08/2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደጀኔ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የ2004 ዓ.ም. የመጀመሪያውን ጉባኤ መጋቢት 22 እና 23 ቀን 2004 ዓ.ም. አካሒዷል፡፡sera amerare meeting 2004

ጉባኤው የሥራ አመራሩ ባለፉት 6 ወራት ያከናወናቸውን የስብሰባና የውሳኔ ቃለ ጉባኤ ማጽደቅ፣ የሥራ አስፈጻሚ 6 ወር ክንውን ሪፖርት፤ በሀገር ውስጥ 42 እና ከሀገር ውጪ የሚገኙ 3 ማእከላትና 4 ግንኙነት ጣቢያዎች፣ የቅዱሳን መካናትና ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ቦርድ፣ የልማት ተቋማት አስተዳደር ቦርድ የ6 ወር ክንውን ሪፖርት ገምግሞአል፡፡

ጉባኤው አክሎም የሥራ አመራር ጉባኤ ጽ/ቤት ያከናወናቸው ተግባራት፣ የኤዲቶሪያል ቦርድ ሪፖርት ያደመጠ ሲሆን የማኅበሩ ኦዲትና ኢንስፔክሽን አገልግሎት አጠቃላይ የማኅበሩን አገልግሎት የተመለከተም የኦዲትና የኢንስፔክሽን ሪፖርት አቅርቧል፤ በቀረበው ሪፖርት ላይም ሰፊ ውይይት ተደርጓል፡፡

የ2004 ዓ.ም. የመጀመሪያው የ6 ወር ጉባኤ ላይ በአጀንዳነት በቀረቡት የኤዲቶሪያል ቦርድ ፖሊሲ፣ የጽ/ቤት ግንባታ ሒደት፣ የሒሳብና ገቢ አሰባሳቢ፣ የቀጣይ 4 ዓመት ስልታዊ እቅድ መነሻና የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ ፕሮግራም እና የማኅበሩ 20ኛ ዓመት የበዓል አከባበር በተመለከተ ውይይት አድርጓል፡፡
በሁለተኛው ቀን ጉባኤ ላይ ለተወሰነ ሰዓት የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሓላፊ በጉባኤው ላይ ተገኝተዋል፡፡ ሓላፊው ቆሞስቆሞስ መላከ ጽዮን አባ ኅሩይ ወንድይፍራው መላከ ጽዮን አባ ኅሩይ ወንድ ይፍራው በቀረቡት ሪፖርቶችና አጠቃላይ በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ማኅበሩ እያደረገ ያለውን አገልግሎት የቤተ ክርስቲያናችን ሕግና ሥርዓት የማኅበሩም ሕግ በሚፈቅደው መሠረት መሥራትና አጠናክሮ እንዲቀጥል አባታዊ ምክር አስተላልፈዋል፡፡ በተጨማሪም “ከዚህ በኋላ ቅዱስ ሲኖዶስ የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያውን ችግር እንደችግር አያነጋግርም፡፡ መፍትሔው ሕጉን በመጠበቅ በመምሪያው እየተሰጠ ነው የሚሔደው፡፡ ሌላው ጥቃቅን የቤተ ክርስቲያን ችግር ቢፈጠር እንኳን በውይይት ይፈታል በወረቀት የሚፈታ አይደለም ይህንን እኔ አምናለሁ…”
ለሁለት ቀናት በታየው በዚህ ጠቅላላ ጉባኤ ከሀገር ውስጥ የ39 ማእከላት ተወካዮችና ከሀገር ውጪ የካናዳ ማእከል እና የማኅበሩ ሥራ አመራርና ሥራ አስፈጻሚን ጨምሮ የኦዲትና ኢንስፔክሽንና የኤዲቶሪያል ቦርድ ሓላፊዎች ተገኝተዋል፡፡

ሰሙነ ሕማማት(ዘረቡዕ)

በመምህር ኃይለማርያም ላቀው

 

በቅዱስ ማቴዎስና በቅዱስ ማርቆስ አዘጋገብ መሠረት ሦስት ነገሮች በዕለተ ረቡዕ ተደርገዋል፤ እነርሱም የሚከተሉት ናቸው፡፡

1.    የካህናት አለቆች÷ የሕዝብ ሽማግሌዎችና ጸሐፍት ፈሪሳውያን በጌታችን ላይ  ተማክረዋል፤

2.    ጌታችን በስምዖን ዘለምጽ ቤት ሳለ አንዲት የተጸጸተች ሴት ሽቱ ቀብታዋለች፡፡

3.    ከዳተኛው ይሁዳ ጌታችንን አሳልፎ ለመስጠት ከጸሐፍት ፈሪሳውያንና ከካህናት አለቆች ዘንድ 30 ብር ተመዝኖለታል፡፡

የካህናት አለቆችና የሕዝብ ሹማምንት በጌታችን ላይ ይሙት በቃ ለመወሰን የሰበሰቡት ሸንጐ “ሲኒሃ ድርየም” ይባላል፡፡ በዚህ ሸንጐ ላይ በአብዛኛው የተሰየሙት ሰዱቃውያን ሲሆኑ የተቀሩቱ ደግሞ ጸሐፍት ፈሪሳውያን ነበሩ፡፡ ሸንጐው በአጠቃላይ 72 አባላት የነበሩት ሲሆን የሚመራው በሊቀ ካህናቱ ቀያፋ ነበር፡፡

 

በዕለቱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን እንዴት ይዘው እንደ ሚገድሉት መክረዋል፡፡ ከዳተኛው ይሁዳ በጸሐፍት ፈሪሳውያንና በካህናት አለቆች ዘንድ ይጉላላ የነበረውን ጥላቻ ያውቁ ስለነበር “ምን ልትሰጡኝ ትወዳላችሁ እኔም አሳልፌ እሰጣችኋለሁ” በማለት ጌታችን አሳልፎ ሊሰጣቸው እንደሚችል ተዋውሏል፡፡ የአስቆሮቱ ይሁዳ ጌታችን ያስተምር በነበረበት ወቅት ከተለያዩ ሰዎች የሚገባውን ገንዘብ ሰብሳቢ /ዐቃቤ ንዋይ/ ነበር፡፡ ከሚሰበሰበው ሙዳየ ምጽዋት ለግል ጥቅሙ እየቀረጠ የማስቀረት የእጅ አመል ነበረበት፡፡ ይሁዳ ፍቅረ ንዋይ እንደሚያጠቃው ድብቅ አመሉ ጎልቶ የወጣው ጌታችን በለምጻሙ በስምዖን ቤት ሳለ አንዲት ሴት ዋጋው ውድ የሆነ ሽቱ በቀባችው ጊዜ ይሁዳ የተቃውሞ ድምፅ ካሰሙት አንዱ ነበር፡፡  “ይህ ሽቱ ተሽጦ ለድሆች ቢሰጥ መልካም ነበር” በማለት ያቀረበው ሐሳብ “አዛኝ መሳይ ቅቤ አንጓች” እንደ ሚባለው ነበር፡፡ ሽቱ ሲሸጥ የሚያገኘው ጥቅም አለ፤ ሽቶ ከፈሰሰ የሚተርፈው የለም፡፡ ይህ በመሆኑ ተቆርቋሪ መስሎ ያቀረበው ሐሳብ ተቀባይነት ስላጣ ማኩረፊያ ያገኘ መስሎት በቀጥታ ከካህናት አለቆች ዘንድ ሄዶ ተዋዋለ፡፡ ብር 30 ተመዘነለት፡፡ ይህ አሳዛኝ ታሪክ በሦስቱ ወንጌላት ውስጥ በሚከተሉት ጥቅሶች ቀጽፎ እናገኛለን፡፡ ማቴ.26÷3-16፤ ማር.14÷1-11፤ ሉቃ.22÷1-6 ይመልከቱ፡፡

 

የአስቆሮቱ ይሁዳ እንደ ሌሎች ሐዋርያት ከጌታችን እግር ስር ተምሯል፡፡ በረከተ ኅብስቱን ተመግቧል፡፡ የተለያዩ ገቢረ ተአምራት በጌታችን እጅ ሲደረጉ ሁሉ ተመልክቷል፡፡ ጌታችንም ከሌሎቹ ሁሉ ሳይለየው እግሩን አጥቦታል፤ ከዳተኛው ይሁዳ ግን ለሐዋርያነት የጠራውን ተንበርክኮ እግሩን ያጠበውን ጌታውን አሳልፎ ሰጥቷል፡፡ “የሰው ልጅስ ስለ እርሱ እንደ ተጻፈ ይሄዳል÷ ነገር ግን የሰው ልጅ አልፎ ለሚሰጥበት ለዚያ ሰው ወዮለት እንደ ተባለ፡፡” ማቴ.26÷24፡፡ ሌሎች ሐዋርያት ከጌታችን ዘንድ ፍቅሩን ገንዘብ ሲያደርጉ ይሁዳ ግን እርግማንን ነው ያተረፈው፡፡ “ገንዘብ የኃጢአት ስር ነው” ተብሎ አንደ ተነገረ ይህ የኃጢአት ስር የክርስቲያኖችን ሕይወት ሊያደርቅ ስለሚችል ለገንዘብ ያለን ፍቅር በልኩ ሊሆን ይገባል፡፡ ሰው ይህን ህልም ቢያተርፍ ነፍሱን ከጐዳ ምን ይጠቅመዋል ተብሎ የተነገረውን ቃል ልብ ማለት ጠቃሚ ነው፡፡

 

ክርስቲያን ነን በማለት የክርስትናውን ስም በመያዝ እምነታቸውን፣ የቆሙበትን ዓላማ በመገንዘብ የሚለውጡ ሰዎች ዛሬም እንደ ይሁዳ ጌታችንን እየሸጡት እንደሆነ ሊገነዘቡ ይገባል፡፡ ለድሆች መመጽወት ክርስቲያናዊ ግዴታ ነው፡፡ ዳሩ ግን በድሆች ስም የሰውን ገንዘብ ለግል ጥቅም ማዋል እጅግ የከፋ ኃጢአት ነው፡፡ እንደዚህ ዓይነት ሰዎች ለገንዘብ ብለው ድሆችን ለረሃብ ለችግር ባልንጀራቸውን ለመከራ እና ለሞት አሳልፈው ሲሰጡ ምንም አይጸጽታቸውም፡፡ እውነተኛ ክርስቲያኖች ግን ሕይወታችንን ለገንዘብ ፍቅር ሳይሆን ለእምነታችንና ለባልንጀራችን አሳልፈን መስጠት ይኖርብናል፡፡ በፍቅረ ንዋይ ተጠምደን ሰዎችን አሳልፎ በመስጠት ለአይሁዳዊ ሸንጐ ምቹ ሆነን መገኘት እንደሌለብን መገንዘብ አለብን፡፡

ሰሙነ ሕማማት ( ዘሰሉስ)

ማክሰኞ

በዚህ ዕለት ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱሱ ክርስቶስ ስለ ሥልጣኑ ተጠይቋል፡፡ ጠያቂዎቹ የካህናት አለቆችና የሕዝብ አለቆች ናቸው፡፡ ጥያቄውም በማን ሥልጣን እነዚህን ታደርጋለህ? ይህንስ ሥልጣን የሰጠህ ማነው?€ የሚል ነበር፡፡ የካህናት አለቆች ያቀረቡት ጥያቄ ነበር፡፡ ጌታችን ሰኞ ዕለት ሁለት ነገሮችን ማድረጉን ተያይዞ የተነሣ ጥያቄ ነው፡፡ ሰኞ ከቅጠል ብቻ በቀር ፍሬ ያላገኘባትን ዕፀ በለስ ረግሟል፤ በማስከተል ወደ ቤተ መቅደስ ገብቶ የሚሸጡትንና የሚለውጡትን አስወጥቷል፡፡ ማቴ.21:23-25፤ ማር.11:27፣ ሉቃ.20·1-8፡፡ ከላይ እንደ ተገለጸው ጌታችን ሲያደርጋቸው የነበሩት ተአምራትና የኃይል ሥራዎች የካህናት አለቆችን ስላስቀናቸው ጌታችንን ከሮማ መንግሥት ባለ ሥልጣናት ጋር ለማጋጨት የቀየሱት ስልት ነው፡፡

ጌታችን በቤተ መቅደስ የነበሩትን ነጋዴዎችን አባሯል፤ መደባቸውን ገለባብጧል፡፡ ነጋዴን ማባረርና መደብን ማስለቀቅ መንግሥታዊ ሥራ ነው፡፡ በአንድ አገር የንግድ ቦታን የሚያጸድቅ መንግሥት መሆኑ እሙን ነው፡፡ ጌታችን ፈሪሳውያን ላቀረቡት ጥያቄ ቀጥተኛ መልስ አልመለሰም፡፡ ምክንያቱም ጥያቄው ለከሳሾቹ አመቺ ሁኔታን ስለሚፈጥር ጥያቄውን በጥያቄ መልሷል፡፡ በመባሕተ መኑ ትገብር ዘንተ፤ በማን ሥልጣን ነው ይህን የምታደርገው? ነበር ያሉት፡፡ በራሴ ሥልጣን ቢላቸው ፀረ መንግሥት አቋም አለው በማለት ከሮማ መንግሥት ዘንድ ለማሳጣት ነበር ዕቅዳቸው፡፡

ጌታችን እኩይ የሆነውን የፈሪሳውያንን አሳብ በመረዳት œየዮሐንስ ጥምቀት ከየት ነው ከሰማይ ነው ወይስ ከምድር ሲል ጠይቋቸዋል፡፡ ከሰማይ ያልነው እንደ ሆነ ለምን አላመናችሁበትም ይለናል:ከሰው ያልነው ከሆነ ሕዝቡ ይጣላናል፡፡ ምክንያቱም ሕዝቡ ዮሐንስን እንደ አባት ይፈሩት እንደ መምህር ያከብሩት ነበርና ሕዝቡን እንፈራለን ተባብለው ከወዴት እንደሆነ አናውቅም ብለው መለሱለት፡፡ እርሱም እኔም በማን ሥልጣን እነዚህን እንደማደርግ አልነግራችሁም አላቸው፡፡ ይህንንም መጠየቃቸው እርሱ የሚያደርጋቸውን ሁሉ በራሱ ሥልጣን እንዲያደርግ አተውት አልነበረም፣ ልቡናቸው በክፋና በጥርር ስለተሞላ እንጂ፡፡ 

በማቴ.21፡28፤ 25፡46፤ ማር.12፡2፤ 13፡37፤ ሉቃ.20፡9፤ 21፡38 የሚገኙት ትምህርቶች ሁሉም የማክሰ ትምህርት ባላሉ፡፡ በዚህ ዕለት በቤተ መቅደስ ረጅም ትምህርት ስላስተማረ የትምህርት ቀንም ባላል፡፡ ክርስቲን የሆነ ሁሉ ከሥጋዊ ነገር ርቆ በዚህ ሰሞን የሃማኖት ትምህርት ሲማር ሲይቅ መሰንበቱ መጽሐፋዊ ሥርዓት ነው፡፡

ዛሬም ቢሆን መልካም ሥራን በሠራን ጊዜ ከልዩ ልዩ ወገኖች የሚመጡ ፈተናዎች ለመልካም ሥራችን እንቅፋት ሊሆን እንደሚችሉ መገንዘብ አለብን፡፡ ብዙ ወገኖች ለቅን አሳባችን ለምን ሰዎች ክፉ ነገር ይመልሱልናል በማለት ሲጠይቁ ይሰማል፡፡ ለቅን ዐሳባችን ከዓለም ዘንድ የተገላቢጦሽ ነገር እንደ ሚጠብቀን ዓለም የሚወደው የገዛ ወገኑን ነው የሚለውን የጌታችንን ትምህርት ልብ ይሏል፡፡ ይህ በመሆኑ በዘመናችን አሳልፈው ሊሰጡን የሚፈልጉ ሰዎች ፈታኝ ጥያቄ እንደሚያቀርቡልን ከወዲሁ ልንገነዘብ ይገባል፡፡

ሰሙነ ሕማማት

ሚያዝያ 1/2004 ዓ.ም. 

መምህር ኃይለ ማርያም ላቀው

ፍቅር የተከፈለ የመሥዋዕትነት ሥራ ስለ ተሠራበት፣ የሰው ልጆች ደኅንነት ስለ ተፈጸመበት፣ መድኀኔዓለም ስለ እኛ ቤዛ ሆኖ ለመስቀል ሞት ታዛዥ ሆኖ ነፍሱን ስለ ካሠልን “ቅዱስ ሳምንት” ተብሏል፡፡ በተጨማሪም “የመጨረሻ ሳምንት” ተብሎ ይጠራል፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ዓለም በሙዓለ ሥጋዌው ለፈጸማቸው የቤዛነትና የአርአያነት ተግባራት ፍጻሜ በመሆኑ ነው፡፡

በዚህ ልዩ በሆነ ሳምንት ካህናትና ምእመናን በነግህ፣ በሠልስት፣ በቀትር፣ በተሰዓትና በሠርክ ወደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በመጓዝ ስለ ጌታችን ኢየስስ ክርስቶስ ሕማማተ መስቀል የሚያዘክረውን ምዕራፍ ከቅዱሳት መጻሕፍት በማንበብና በመጸለይ ሕማሙንና ሞቱን ያዘክራሉ፤ ቅዱስ ያሬድ በመጨረሻው ሳምንት በየዕለቱ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ላይ የተፈጸመውን ነገረ መስቀል በተመለከተ ያዘጋጀውን መዝሙር ይዘምራሉ፤ አብዝተው ስግደትን ይሰግዳሉ፡፡

 

ሰሙነ ሕማማትን ከሌሎች የዐቢይ ጾም ሳምንታት ልዩ የሚያደርገው ሥርዓት አለ፡፡ በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት ሥርዓትና ደንብ መሠረት በሰሙነ ሕማማት ከጸሎተ ሐሙስ በስተቀር ቅዳሴ አይቀደስም፣ ስብሐተ ነግህ አይደረስም፣ ጸሎተ ፍትሐት አይጸለይም፣ ጸሎተ አስተስርዮም አይደረግም፡፡ እንዲሁም ጥምቀተ ክርስትናም አይፈጸምም፡፡ ከላይ የተዘረዘሩት የቤተ ክርስቲያን ሥርዓቶች አስቀድሞ በዕለተ ሆሳዕና ይከናወናሉ፡፡

 

በተጨማሪም ማንኛውም ክብረ በዓል በዚህ ሳምንት ቢውል ከትንሣኤ በኋላ እንዲከበር ይተላለፋል፡፡ ይህ ብያኔ በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት ዘንድ የጸና ኦርቶዶክሳዊ ሥርዓት ነው፡፡ ሕማምና ሞት የማይገባው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የእኛን ሕማምና ሞት ለራሱ በማድረግ በዚህ ሳምንት ለእኛ ቤዛ ሆኗል፡፡ “ደዌያችንን ተቀበለ፤ ሕማማችንንም ተሸከመ፤ ከዓመፀኞችም ጋር ተቆጠረ፡፡ እርሱ ግን ግፍን አላደረገም ተንኮልም በአፉ አልተገኘበትም፡፡” /ኢሳ.53÷4-12/ ተብሎ እንደ ተጻፈ፡፡ ምእመናን ክርስቶስ የተቀበለው የእኛን ሕማም መሆኑን በማዘከር በሰሙነ ሕማማት ከማንኛውም የሥጋ ሥራ መታቀብ ዋዛ ፈዛዛ ባለመነጋገር በኀዘን ልናከብረው ይገባል፤ ብድራትን የማያስቀረው አምላክም መተላለፋችንና በደላችንን በመደምሰስ የመንግሥቱ ወራሽ ያደርገናልና፡፡

 

ሰሙነ ሕማማት አስከ አራተኛው ምዕተ ዓመት ድረስ ከጾሙ ተለይቶ ለብቻው ይከበር ነበር፡፡ በኋላ ግን በባሕረ ሐሳብ ቀመር መሠረት ጾሙም ሕማማቱም ትንሣኤውም ተያይዘው እንዲከበሩ ተደረገ፡፡ ምዕራባውያን ከአርባ ጾም ውስጥ የመጨረሻውን ሳምንት ሰሙነ ሕማማት ያደርጉታል፡፡ የምሥራቃውያን /ኦሪየንታል/ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት ግን አርባውን ጾም ጨርሰን ከኒቆዲሞስ በኋላ ያለውን ተከታዩን አንድ ሳምንት ሰሙነ ሕማማት አድርገን እናከብራለን፡፡ከእነዚህ የሕማማት ሳምንት ውስጥ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሦስቱ ዕለታት /በሰኞ፣ ማክሰኞ እና ረቡዕ/ ያከናወናቸው የድኅነት ሥራዎች የሚከተሉት ናቸው፡፡

 

ሰኞ

ጌታችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው ሆኖ በዚህ ዓለም ሲመላለስ በሆሳዕና ማግሥት ጌታችን ከቢታንያ ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባ ሁለት ነገሮችን አድርጓል፡፡ አንደኛ ከቅጠል በስተቀር ፍሬ ያልተገኘባትን ዕፀ በለስ ረግሟል፡፡ ሁለተኛ ወደ ቤተ መቅደስ ገብቶ የሚሸጡትንና የሚለውጡትን አስወጥቷል፡፡/ማቴ.21÷12-17፤ ማር.11÷17፤ ሉቃ.19÷45-46፡፡/ በቅዱስ ማቴዎስ አገላለጥ “በማግሥቱ ተራበ” የሚል ቃል እንመለከታለን፡፡

 

ነቢዩ ኢሳይያስ “እግዚአብሔር ለዘለዓለም አይራብም፤ አይጠማም፤ አይደክምም” /ኢሳ.46÷25/ ይላል፡፡ በቅዱስ ወንጌልም “በመጀመሪያ ቃል ነበር” ይላል፡፡ ያ ቃል ቀዳማዊ እንደ ሆነ፣ ቃል በእግዚአብሔር ዘንድ እንደ ነበር፣ ያም ቃል እግዚአብሔር ነው ተብሎ ተጽፏል፡፡ ዮሐ.1÷1-2፡፡ ጌታችንም በመዋዕለ ትምህርቱም ሲያስተምር “የእኔስ መብል የላከኝን የአባቴን ፈቃድ አደርግ ዘንድ፡ ሥራውንም እንፈጽም ዘንድ ነው” /ዮሐ.4÷34/ ሲል ተናግሯል፡፡ ነቢዩ እግዚአብሔር እንደማይራብ ተናግሯል፡፡ ታዲያ ጌታችን ለምን ተራበ?

 

ሰማያውያን መላእክት እንዳይራቡ አድርጎ የፈጠረ፣ እስራኤልን ገበሬ በማያርስበት፣ ዘር በሌለበት፡ ዝናብ በማይጥልበት ምድረ በዳ የመገበ ፤ድኅረ ሥጋዌ በአምስት አንጀራና በሁለት ዓሣ ከ5000 የሚበልጡ ሰዎችን የመገበ ተራበ! ተብሎ ሲነገር እጅግ ይደንቃል፡፡ በእርግጥ ፍጹም አምላክ ፍጹም ሰው በመሆኑ አልተራበም አንልም፡፡ የጌታችን ረሃብ ንዴት ያለበትና የአንዲት የበለስ ዘለላ ረሃብ አይደለም፡፡ ረሃቡ የበለስ ፍሬ ሳይሆን “በለስ ብሂል ቤተ እስራኤል እሙንቱ” እንዲል የሃይማኖትና የመልካም ሥነ ምግባርን ፍሬ የሻ መሆኑን ለማጠየቅ ነው፡፡ ጌታችን የፈለገውን ባለማግኘቱ ጉባኤ አይሁድን ረግሟል፡፡ በአይሁድ ጉባኤ የነገሠውን ኃጢአት፤ በበለስ አንጻር መርገሙን ታላቁ ሊቅ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ “በአንጻረ በለስ ረገማት ለኃጢአት፤በበለስ አንጻር ኃጢአትን ረገማት” ብሏል፡፡

 

እስራኤልም በአንድ ወገን የተጠበቀባቸውን ፍሬ ባለማፍራታቸው ተረግመዋል፡፡ ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እስራኤል ከፍቅር ይልቅ እርግማን እንዳገኛቸው አሕዛብ ደግሞ የቃሉን ትምህርት ሰምተው የእጁን ተአምራት አይተው የአመኑበትን የእግዚአብሔር የጸጋ ልጁ ለመሆን መብቃታቸውን ሲመሰክር እንዲህ ይላል፡- “አሕዛብ አስተጋብኡ ጽጌሬዳ በኂሩቱ ወሶኩሰ ተርፈ ኀበ አይሁድ ዘውእቱ ሕፀተ ሃይማኖት፤ አሕዛብ በእግዚአብሔር ቸርነት አበባ ሰበሰቡ፤ በአይሁድ ዘንድ ግን እሾኹ ተረፈ፡፡ ይኽውም የሃይማኖት ጉድለት ነው፡፡” ብሎ ተርጉሞታል፡፡ እሾኽ የእርግማን ምሳሌ ነው፤ አበባ የእግዚአብሔር ጸጋ ልጅነት ምሳሌ ነው፡፡ ዛሬ የእግዚአብሔር ቤተሰቦች ጌታችን ወደ መቅደስ ሕይወታችን ቢመጣ ምን ያገኝ ይሆን? ፍሬ ወይስ ቅጠል? የእግዚአብሔር ቃል ግን ለንስሐ የሚገባ ፍሬ አድርጉ ይለናል፡፡ ማቴ.3÷8፡፡ ስለዚህ እግዚአብሔር ከእኛ የሚፈልገውን የመንፈስ ቅዱስ ፍሬ እናፍራ፡፡ ገላ.5÷22፡፡ ጌታችን በዳግም ልደት ሲመጣ ከሰው ልጅ ሃይማኖት መገኘቱ አጠራጣሪ እንደሆነ ተናግሯል፡፡ “የሰው ልጅ ወደዚህ ዓለም ሲመጣ ሃይማኖት ያገኝ ይሆንን?” ቀጣይ ሕይወታችንን በአምላካዊ ሥልጣኑ የቃኘ አምላክ በመጣ ጊዜ የእምነት ፍሬ አፍርተን ከእግዚአብሔር ዘንድ ዘላለማዊ ፍቅሩን ለማትረፍ እንትጋ፡፡

የቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያንን ዳግም ለማነጽ የገቢ ማሰባሰቢያ ተካሔደ

መጋቢት 28/2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

በቅርቡ በአክራሪ ሙስሊሞች ሙሉ ለሙሉ ወደተቃጠለው በስልጤና ሃዲያ፣ ጉራጌ ከንባታ ሀገረ ስብከት ጋራሬ ቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያን መጋቢት 23/2004 ዓ.ም. መንፈሳዊ ጉዞ ተካሔደ፡፡ የጉዞው ዓላማ በቃጠሎው ምክንያት የተጎዱትንና ተስፋ በመቁረጥ ላይ የሚገኙትን የአካባቢውን ምእመናንን በቃለ እግዚአብሔር ለማጽናናት ቤተ ክርስቲያኑን ዳግም ለማነጽ እንዲረዳ የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር ለማካሔድ ታስቦ የተዘጋጀ ነበር፡፡

አዲስ አበባ በሚገኘው በማኅበረ ነህምያ የስልጤ ዞን አብያተ ክርስቲያናት መርጃ ማኅበር ከሥልጤ አካባቢ ተወላጆች ጋር በመተባበር የተዘጋጀ ጉዞ ሲሆን በተጨማሪም በአዋሳና ሻሸመኔ የሚገኙ ምእመናን ቤተ ክርስቲያኗ ያለችበት ሁኔታ ለማየትና የአቅማቸውን አስተዋጽኦ ለማድረግ በቦታው ተገኝተዋል፡፡

 

በሥፍራው ከተገኘው ማኅበረ ምእመናን በተደረገው የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር በጥሬ ገንዘብ ከ200,000 /ሁለት መቶ ሺህ ብር/ በላይ ሊሰበሰብ ችሏል፡፡ በተጨማሪም ገንዘብና ጥሬ እቃ ለማቅረብ ከምእመናን ቃል የተገባ ሲሆን በዕለቱ በተጋበዙ መምህራነ ወንጌል የማጽናኛ ትምህርት የተሰጠ ሲሆን ያሬዳዊ ዝማሬም ቀርቧል፡፡

 

ከሥፍራው ያገኘነው መረጃ እንደሚጠቁመው ከመንግሥት በተሰጠው ውሳኔ መሠረት ቤተ ክርስቲያኑን ለመሥራት ተለዋጭ ቦታ የተሰጠ ሲሆን የይዞታ ማረጋገጫም ለማግኘት ተችሏል፡፡ የቀድሞው ቤተ ክርስቲያን ይዞታ አሁን ከተሰጠው ቦታ ድንበር ላይ የሚገኝ ሲሆን ለጥምቀተ ባህር ቤተ ክርስቲያን  እንድትጠቀምበት ውሳኔ አግኝቷል፡፡

 

የአካባቢው ምእመናን ከጎናቸው መሆናቸውን ለመግለጽና ለማጽናናት የመጡትን ምእመናን አመስግነው በተካሔደው መርሐ ግብር እንደተደሰቱ በመግለጽ ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡ በዕለቱ ከ1500 በላይ ምእመናን በመርሐ ግብሩ ላይ ተሳትፈዋል፡፡

 

የጋራሬ ቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያንን ዳግም ለማነጽ ግንቦት 5/2004 ዓ.ም. የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ አቡነ ቀሌምንጦስ  የመሠረት ድንጋይ ያኖራሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡

ከ175 በላይ በገና ደርዳሪዎች ይመርቃሉ፡፡

መጋቢት 26/2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደጀኔ

በማኅበረ ቅዱሳን ልማት ተቋማት አስተዳደር የአቡነ ጎርጎርዮስ የትምህርትና ሥልጠና ማእከል ከ175 በላይ በገና ደርዳሪዎችን መጋቢት 29 ቀን 2004 ዓ.ም. እንደሚያስመርቅ አስታወቀ፡፡

የትምህርትና ሥልጠና ማእከሉ ሓላፊ አቶ አብዮት እሸቱ እንደገለጹት ማኅበረ ቅዱሳን ከዚህ በፊት በዜማ ማሠልጠኛ ክፍሉ በርካታ በገና ደርዳሪዎችን ማስመረቁን ገልጸው የአሁኖቹን ተመራቂ ጨምሮ ከ1200 በላይ በገና ደርዳሪዎቹን በማእከሉ ማሠልጠኑን ገልጸዋል፡፡

 

መጋቢት 29 ቀን 2004 ዓ.ም. በጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ ከቀኑ 7፡30 በሚካሔደው የምረቃ መርሐ ግብር ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የተመራቂ ቤተሰቦችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች እንደሚገኙ የገለጹት የማእከሉ ሓላፊ ማኅበረ ቅዱሳን ቅዱስ ሲኖዶስ በሰጠው መተዳደሪያ ደንብ መሠረት የቤተ ክርስቲያንን እምነት፣ ሥርዐት፣ ትውፊትና ዶግማ ተጠብቆ ወደ ቀጣዩ ትውልድ ለማስተላለፍ የተሰጠውን ሓላፊነት እየተወጣ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

 

የአቡነ ጎርጎርዮስ የትምህርትና ሥልጠና ማእከል በአሁኑ ወቅት ከ KG እስከ 9ኛ ክፍል ተማሪዎችን በቀለም ትምህርት እያስተማረ የሚገኝ ሲሆን በዜማና በአብነት የትምህርት መስክ ሥልጠናዎችን እየሰጠ እንደሚገኝ አቶ አብዮት ገልጸዋል፡፡

የዐብይ ጾም ስብከት /ክፍል 7/

መጋቢት 26/2004ዓ.ም.

በአያሌው ዘኢየሱስ


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤


ብፁዕ አቡነ መልከ ጼዴቅ የከምባታ፣ ሀድያ፣ ጉራጌና ስልጢ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤በአዲስ አበባ የደብረ ብሥራት ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን የበላይ ኃላፊ፤ቀደም ሲል በዚሁ ደብር አስተዳዳሪ ሆነው ባገለገሉባቸው ዓመታት ውስጥ ለማጠቃለያ ከሰበኳቸው በርካታ የወንጌል ስብከቶች መካከል የተወሰደ፡፡/መጋቢት 21 ቀን 1985 ዓ.ም./

እውነት እውነት እልሃለሁ፡- ሰው ዳግመኛ ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ የእግዚአብሔርን መንግሥት አያይም፡፡ ጌታችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይህንን የተናገረው ለኒቆዲሞስ ነው፡፡

ኒቆዲሞስ የሃይማኖት ሊቅ ነው፡፡ ብዙ የተማረ ብዙ ያወቀ ሰው ነው፡፡ ከዚህም የተነሣ ሊቅ – ምሁር – አለቃ ተብሎ ተጠርቶአል፡፡ በጊዜው ከነበሩ ሰዎች ከፍ ያለና የላቀ ዕውቀት የነበረው ሰው ነበር፡፡ በሌሊት ወደ ጌታ እየመጣ ይማር ነበር፡፡ የማታ ተማሪ ነበር፡፡ ቀን – ቀን የምኩራብ አስተማሪ ሆኖ ብዙ ሰዎችን ያስተምር ስለ ነበረና እርሱ የሚያስተምራቸው አይሁድ ጌታን ስላልተቀበሉ ቀን ለቀን መጥቶ የሚማርበት አመቺ ጊዜ አልነበረውም፡፡

በአይሁድ ሕግ ጌታን የሚከተልና የሚቀበል ሰው ከምኲራብ የሚባረር ስለሆነ እነርሱን ላላማስቀየም ማታ ነበር የሚማረው፡፡ ኒቆዲሞስ ለጌታ ከሰው ችሎታ በላይ የሆኑ ተአምራትን ስለምትሠራ እኛን ለማስተማርና ለመምከር ከእግዚአብሔር ዘንድ ተልከህ የመጣህ ነህ ብሎ መስክሮለታል፡፡ ጌታም ለእናንተ ተልኬ የመጣሁ ከሆነና እናንተን ለማስተማር እንደ መጣሁ ከተረዳህ ሰው ዳግመኛ ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት አይገባም አለው፡፡

ኒቆዲሞስ ስላልገባው እኔ አርጅቼአለሁ፤ እንዴት ነው ወደ እናቴ ማኅጸን ተመልሼ የምገባውና ዳግም የምወለደው? ብሎ ኢየሱስ ክርስቶስን ጠየቀው፡፡ ጌታም፡- ሰው ከሰው ከተወለደ ሥጋዊ ነው፤ የሰው ልጅ ነው፡፡ የእግዚአብሔር ልጅ ለመሆን በመንፈስ መወለድ አለበት፡፡ ከእግዚአብሔር መወለድ ነፋስ ከየት ተነሥቶ ወዴት እንደሚነፍስ እንደማይታወቅ ያለ ረቂቅ ምሥጢር ነው አለው፡፡ አሁንም ያ ሊቅ፤ ያ አዋቂ አልገባኝም አለ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስም፡- አንተ የእስራኤል ሊቅና አዋቂ ሆነህ እንዴት ይህን አታውቅም አለው፡፡ ከሰማይ ከወረደው በቀር ወደ ሰማይ የሚወጣ የለም፤ የምናውቀውንም እንናገራለን ካለው በኋላ ጥያቄውን በዚህ ገታ፡፡

ኒቆዲሞስ  ወደ ጌታችን ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ መጥቶ መማሩ የምያስመሰግነው ተግባር ነው፡፡ አይሁድ ወገኖቹ ጌታን ሳይከተሉት እርሱ ጌታን መውደዱ የሚያስደንቅ ነው፡፡ ኒቆዲሞስ የሚያመሸው ከጌታ ጋር ነበር፡፡ ባለችው ትርፍ ጊዜው ሁሉ ወደ ፈጣሪው ይሔድ ነበር፡፡ ይህ ታላቅ ዕድል ነው፡፡ ቀን ሲያስተምርና ሲደክም ስለሚውል ማታ – ማታ ማረፍ ይገባው ነበር፡፡ ኒቆዲሞስ ግን ቤቴ ገብቼ ልረፍ አላለም፡፡ ባለ ሥልጣንና ባለጸጋ ስለ ነበር ደጅ የሚጠናው ሕዝብና መሰል ባልንጀሮቹ ይፈልጉት ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ከእነርሱ ጋር አላመሸም፡፡

ከዚህ አባት ታላቅ ትምህርት ልንማር ያስፈልጋል፡፡ እኛ ዛሬ የምናመሸው የት ነው? የምናመሸውስ ከማን ጋር ነው? ምን ስናደርግ ነው የምናመሸው? ኒቆዲሞስ ቤቱ አልነበረም የሚያመሸው፤  ከእውነተኛው መምህር ጋር እንጂ፡፡ ኒቆዲሞስ ጽድቁንና በረከቱን እየያዘ ነበር ወደ ቤቱ ይገባ የነበረው፡፡ እኛ ወደ ቤታችን የምንገባው እየከበርን ነው ወይ? ጸድቀን ነው የምንገባው ወይስ ጎስቁለን?

የዛሬው ሰው እየሰከረ፣ እየጨፈረ፣ እየደማ፣ እየቆሰለ አብዶ ነው የሚመለሰው፡፡ በቤት ያሉትም እንቅፋት ያገኘው ይሆን? ይሞት ይሁን? እያሉ እየተሳቀቁ ነው የሚያመሹት፡፡ የሚሞትም አለ፡፡ ማምሸት እንደ ኒቆዲሞስ ከጌታ ጋር ነው እንጂ! ኒቆዲሞስ ከጌታ ጋር በማምሸቱ ፈጣሪውን አወቀ፡፡ ጌታን ማወቅ ብቻ ደግሞ አይበቃም፡፡ ማወቅማ አጋንንትም ያውቁታል፡፡ ከመንፈስ መወለድ መወለድ ያስፈልጋል፡፡

ሰው ዕፀ በለስን በበላ ጊዜ የእግዚአብሔር ልጅነቱን ተነጥቆ ነበር፡፡ ጌታ መጥቶ ዳግም ሰው እስከሚያደርገን ድረስ የሰይጣል ልጆች ሆነን ነበር፡፡ ከዚያም በአርባና በሰማኒያ ቀን ከአብራከ መንፈስ ቅዱስና ከማኅፀነ ዮርዳኖስ ተወልደናል፡፡ አባታችን የምንለው ለዚህ ነው፡፡ ከእርሱ ከተወለድንና ልጅነትን ካገኘን እንደገና ልጅነታችንን ካገኘን እንደገና ልጅነታችንን እንዳናጣ አክብረን እንያዘው፡፡ መጀመሪያም አላወቅንበትም ነበር፡፡ አዳም ከገነት የሚወጣ አልመሰለውም ነበር፡፡ ሰይጣን አታሎታል፡፡ እኛም እንደገና እንዳንታለል ልጅነታችን እንዳይሰረዝ እንጠንቀቅ፡፡

የብዙዎቻችን ልጅነት ዛሬ እየተወሰደ ነው፡፡ ልጅነታችንን እያስነጠቅነው ነው፡፡ እነ ኤሳው እየነጠቁን ነው፡፡ ብዙዎች እንደ ያዕቆብ ልጅነታችንን ሊወስዱብን አሰፍስፈዋል፡፡ ሰይጣን እንደ አዳም ሊነጥቀን አሰፍስፏል፡፡ ዛሬ በጣም አርጅተናል፡፡ ኒቆዲሞስ አርጅቶ ነበር፡፡ በጥምቀትና በንስሓ ግን አዲስ ሕይወት አግኝቶአል፤ ታድሷል፡፡ ያረጀው ሕይወቱ ለመለመ፡፡ ያረጀው ሰውነታችንን በሥጋውና በደሙ በንስሓ እናድሰው፡፡ ይህ ከሆነ ነው የእግዚአብሔርን መንግሥት የምንወርሰው፡፡