በገጠር አድባራትና ገዳማት ያለው የመብዐ ችግር አሳሳቢ እንደሆነ ተገለጠ፡፡

26/2004 ዓ.ም.

ተ/ሥላሴ ጸጋ ኪሮስ

•    የመብዐ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር እየተካሔደ ነው፡፡

በጧፍ፣ በዕጣን፣ በዘቢብና በንዋያተ ቅድሳት እጥረት ምክንያት መንፈሳዊ አገልግሎታቸውን ያቋረጡ ገዳማትና የገጠር አብያተ ክርስቲያናትን ለመታደግ “የመብዐ ሳምንት” በሚል የተዘጋጀው የድጋፍ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር ተጀመረ፡፡ በገጠር አድባራትና ገዳማት ያለው የመብዐ ችግር አሳሳቢ እንደሆነም ተገለጠ፡፡

ከትናንትና በስትያ የካቲት 24 ቀን 2004 ዓ.ም በተደረገው የመክፈቻ መርሐ ግብር ላይ የተገኙት የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ ሊቀ ትጉሃን ዶ/ር ሙሉጌታ ስዩም ባስተላለፉት መልእክት “ከዚህ ቀደም ‘ሁለት ልብሶች ያሉት’ በሚል መርሐ ግብር በአብነት ት/ቤቶችና ገዳማት ያለውን የአልባሳት ችግር ለመቅረፍ ምእመናንና የማኅበሩ አባላት እንደተረባረቡ አስታውሰው፣ ኢትዮጵያ ዘወትር ወደ እግዚአብሔር እጆቿን የምትዘረጋባቸው የአባቶቻችን እጆች እንዳይታጠፉ አሁንም መረባረብ አለብን” ብለዋል፡፡

ሊቀ ትጉሃን አያይዘውም፣ እንደ ሌሎች አኃት አብያተ ክርስቲያናት ለወደፊቱ ቅዱስ ሲኖዶስ በደንቡ አጥንቶት ቤተ ክርስቲያናችን ራሷን አደራጅታ መባዎችን ለእግዚአብሔር እንደሚገባ በጥራት አዘጋጅታ ከሌሎች ጥገኝነት የምትላቀቅበት ጊዜ እስከሚመጣ ለጊዜውም ቢሆን ያለውን ችግር መቅረፍ እንድንችል በተለይ በዚህ የፆምና የጸሎት ሠዓት ከእኛ ብዙ ይጠበቃል በማለት አሳስበዋል፡፡

በክብር እንግድነት ተገኝተው መርሐ ግብሩን በይፋ የከፈቱት ብፁዕ አቡነ እንድርያስ የደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል “በጠበበው በር ለመግባት ተጋደሉ” ሉቃ. 13፥24 በሚል ርዕስ ትምህርት ሰጥተዋል፡፡

ብፁዕነታቸው ከትምህርቱ ጋር አያይዘው ባስተላለፉት መልእክት “መብዐ የክርስትና መነሻ፣ የሙታን ማስቀደሻ፣ የክብረ ቅዱሳን መወደሻ ነው፡፡ ተመስጋኙ እግዚአብሔር አመስጋኙ ሰው ቢሆንም፣ እነዚህ ነገሮች ካልተሟሉ ቅዳሴ የለም፤ ቅዳሴ ከሌለ ደግሞ ሠላም የለም፤ ጠለ በረከትም ይቀራል ማለት ነው፡፡ ከተወደሰ ከተቀደሰ ግን ሰዎች ይሰማሉ፣ ይማራሉ፣ ይጸልያሉ፣ ይፆማሉ፤ እግዚአብሔርም ጠለ በረከቱን ይሰጣል፡፡ በዚህ መንገድም በረከት ይገኛል፡፡ የምትሰጡትንም ለእግዚአብሔር አደራ ስጡ” ብለዋል፡፡

“ከሁሉም ከባዱ የችግሩ አካል ክርስትና ማስነሻ መብዐ አለመኖሩ ነው፡፡” ያሉት ብፁዕነታቸው “በ40 በ80 ቀን ተጠምቆ ሥጋወደሙን በምን ይቀበለው?” በማለት በሀዘን ስሜታችውን ገልጠዋል፡፡

እርሳቸው በሚያስተዳድሩት ሀገረ ስብከት ያለውን ነባራዊ ሁኔታ የገለጡት ብፁዕነታቸው “ከአልባሳት ችግር አንፃር የካህናት ባለቤቶች የነበሩ እናቶች ሲሞቱ ሥጋወደሙ ሲቀበሉበት የነበረውን ቀሚሳቸውን መቀደሻ ይሁንልኝ እያሉ ተናዘው ይሞታሉ፡፡ በእናቶች ቀሚስ ነው የሚቀደሰው፡፡ ለክርስትና ማንሻም አንድ ወይም ሁለት ፍሬ ዘቢብ ታሽቶ ነው የሚቀደሰው፡፡ ይኸውም ከአንዱ ወደ ሌላው አጥቢያ የውሎ መንገድ ተጉዘው የሚያስቀድሱ፣ ክርስትናም የሚያስነሱ ብዙዎች ናቸው፡፡” በማለት መራራውንና አሳዛኙን እውነት አስረድተዋል፡፡

መርሐ ግብሩ በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል አዘጋጅነት ከየካቲት 24 እስከ መጋቢት 4 ቀን 2004 ዓ.ም በማኅበሩ ዋና ማዕከል ጽ/ቤት ላይ ይከናወናል፡፡ ምእመናን ከእነዚህ ቀናት በኋላም በክፍሉ ጊዜአዊ እርዳታ አሰባሳቢ አማካኝነት መብዐ ማስገባት እንደሚችሉ ታውቋል፡፡

የዐቢይ ጾም ስብከት (ክፍል 3)

የካቲት 24/2004 ዓ.ም.

በአያሌው ዘኢየሱስ
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመጥምቁ ዮሐንስ እጅ በዮርዳኖስ ወንዝ በተጠመቀ በሦስተኛው ቀን በገሊላ አውራጃ በቃና መንደር ከእናቱ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምና ከአሥራ ሁለት ሐዋርያቱ ጋር በዶኪማስ ቤት ሠርግ ተጠርቶ ነበር፡፡ በዚያም ወይን ጠጅ አልቆባቸው አፍረውና ተሸማቀው የነበሩትን ጋባዦች ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በእናታችን በቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት ውኃውን የወይን ጠጅ አድርጎ በመቀየር ከዕፍረት አድኗቸዋል፤ ክብሩን በመጀመሪያ ተአምሩ ገልጧል፤ ደቀ መዛሙርቱም በእርሱ አምነዋል፤ዮሐ 2፥1-11፡፡

ጌታችን ከዚህ በኋላ የአይሁድ ፋሲካ ቀርቦ ስለ ነበር የሔደው ወደ ኢየሩሳሌም ነበር፡፡ በዚያ የተመለከተው ነገር ግን በዶኪማስ ሠርግ ቤት ውስጥ ከተመለከተው የአክብሮት ጥሪና መስተንግዶ ጋር ሲነጻጸር ፍጹም ተቃራኒ ነበር፡፡ ጌታ ወደ ዳዊት ከተማ ወደ ኢየሩሳሌም ከገባ በኋላ በቀጥታ ያቀናው ወደ ቤተ መቅደስ ነው፡፡
በእኛ ግን እንዲህ አይደለም፡፡ እኛ ከአንዱ ከተማ ተነሥተን ወደ ሌላው ከተማ ስንደርስ ወይም ገና ካለንበት ከተማ ከመነሣታችን በፊት ቅድሚያ ሰጥተን የምናጣራው ወይም የምንጠይቀው ጉዳይ በከተማይቱ ውስጥ ስላለው የተሻለ መኝታ፣ ጥራት ስላለው ምግብና መጠጥ እንዲሁም ተመራጭ ስለ ሆነው ገላ መታጠቢያ ቤት ነው እንጂ በከማይቱ ውስጥ ስላሉት የተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት፣ በዚያ ስለሚሰጡት መንፈሳዊ አገልግሎት ወይም ስለሚገጥሙአቸው የዲያብሎስ ውጊያዎች አይደለም፡፡ ስለሆነም እኛ ከአንድ ከተማ ተነሥተን ወደ ሌላ ከተማ ስንደርስ አስቀድመን ልንጠይቃቸው ስለሚገቡን አንገብጋቢ ጉዳዮች እንድንጠይቅና ወደዚያ ከተማ እንድንደርስ ያበቃንን አምላክ እናመሰግን  ዘንድ በመጀመሪያ መሔድ የሚገባን ወደ ቤተ እግዚአብሔር መሆኑን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሊያስተምረን ወደ ቤተ መቅደስ ሔዷል፡፡

የአይሁድ የፋሲካ በዓል አይሁድ በኀጢአታቸው ምክንያት በግብጽ ምድር ለ430 ዓመታት በባርነት በግፍ ሲገዙ ከቆዩ በኋላ እግዚአብሔር አምላክ እነርሱን በነቢዩ በሙሴ አማካይነት በኀይልና በተለያዩ ተአምራት በማውጣት ይህን የዘላለም መታሰቢያ እንዲሆናቸው አድርጎ የሰጣቸው ታላቅ የመሻገር በዓል ነው፤ ዘጸ 12፡፡ አይሁድ ይህ ታላቅ የእግዚአብሔር በዓል ሊከበር በቀረበበት አጭር ጊዜ ውስጥ ስለ በዓሉ አከባበር እና ሊከናወኑ በሚገባቸው ቅድመ ዝግጅቶች ላይ ባተሌ መሆን ሲገባቸው ለምስጋና፣ ለጸሎት፣ ለተመስጦ፣ ለስግደት፣ መባ ለማቅረብና ለሥርየት በታነጸው ቤተ መቅደስ ውስጥ በሬዎች፣ በጎችና ርግቦች በማስገባትና ከሕዝቡ ጋር ሲነጋገዱበትና ጥቁር ገበያ አድርገው ገንዘብ ሲለዋወጡበት ነበር ኢየሱስ ክርስቶስ ያገኛቸው፡፡ ሊያደርጉ  የማይገባቸውን ነገር ሊያደርጉ በማይገባቸው ቦታ ላይ ሲያደርጉ ነው ያገኛቸው፡፡ ምስጋና፣ ጸሎት፣ ተመስጦ፣ ስግደት፣ መባ ማቅረብና ሥርየት ማግኘት ከዋጋ ውጣ ውረድ፣ ከቀንስ አትቀንስ ክርክር፣ ከጫጫታ፣ ከንጥቂያ፣ ከስድብና ከድብድብ ጋር ምንም ዓይነት መስማማት የለውም፡፡ የቤተ መቅደስን ንጽሕና መጠበቅና ቤተ መቅደስን በከብቶች አዛባና ሽንት ማቆሸሽ ፍጹም የማይገናኙ ድርጊቶች ናቸው፡፡ ጸሎትና ምስጋና በዋጋ ክርክርና በሁካታ መተካቱ እጅግ የሚያሳዝንና የሚያስቆጣ እኩይ ተግባር ነው፡፡

ዛሬም እንዲሁ ነው፡፡ አንዳንዶች ወደ ቤተ ክርስቲያን ከመጡ በኋላ ስለ ንግድና ስለ ገንዘብ ልውውጥ እንዲሁም ገንዘብ ስለሚገኝበት ሁኔታ መከራከራቸውና መንጫጫታቸው ከአይሁድ ክርክርና ጫጫታ ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ ዛሬ ምስጋና ለማቅረብ፣ ጾም ለመያዝ፣ ስግደት ለመስገድ፣ በተመስጦ ለመቆየት፣ መባ ለማቅረብና ኀጢአትን ለንስሓ አባት በመናዘዝ ሥርየት ለማግኘት ክርስቲያን ተብለው የተጠሩ አማኞች እግዚአብሔርን ለማገልገል ይህን ያህል ገንዘብ ክፈሉን፣ የላመና የጣመ ምግብና መጠጥ አቅርቡልን፣ የተደላደለ መኝታ አንጥፉልን፤ድምፃችንን እጅግ አጉልታችሁ አሰሙልን፤ይህን ካላደረጋችሁልን ወይም ይህን ካልከፈላችሁን አናገለግልም እያሉ ሲታበዩ ማየትና መስማት የተለመደ ነገር ሆኗል፡፡ አልፎ ተርፎ በቤተ መቅደስና በቅጽረ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በነገር ቀንስ-አትቀንስ ሁካታና ጫጫታ ለመደራደር መሞከር ከአይሁድ ተግባር ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ ይህ የኢየሱስ ክርስቶስን የቁጣ ጅራፍ የሚያስነሣ ተግባር ነው፤በማይገባው ቦታ ላይ የሚፈጸም የማይገባ ተግባር ነውና፡፡

ባቀረበው ምስጋና፣ ባደረሰው ጸሎት፣ በሰገደው ስግደት፣ በጾመው ጾም፣ በያዘው ንስሓና በሰጠው መባ ተባርኮ፣ ተቀድሶና ሥርየት አግኝቶ በደስታ ወደ ቤቱ መመለስ የሚገባው ምእመን ገንዘብ የሚገኝበትን ወይም በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የገንዘብ መድረክ ስለሚገኝበት ሁኔታ ወይም የእግዚአብሔርን ቤት የንግድና የኑፋቄ ቤት ለማድረግ በመሞከር ተከራክሮና ተንጫጭቶ፤ተጣልቶና ተኮራርፎ መለያይት የሚገባ ነገር አይደለም፡፡ አይሁድ በቤቱ ውስጥ ለፈጸሙት እኩይ ተግባር በንስሓ ተመልሰው ጌታን ይቅርታ ከመጠየቅ ይልቅ ጭራሽ ለደረሰባቸው ቅጣት እርሱን ምልክት መጠየቃቸው አሳዛኝም አሳፋሪ ነገር ነው፡፡ ዛሬም ቢሆን በጥምቀት ልጅነትን፣ በሜሮን መታተምን፣ በንስሓ ሥርየትን፣ በእምነት መንግሥተ ሰማያትን ያሰጠችና የምታሰጥ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን የንግድ ቤት ለማድረግ ሞክረው ያልተሳካላቸው ሰዎች ከጥፋት በፊት ይቅርታ እንዲጠይቁ ታሳስባለች፡፡

ይህ ስለሆነ ነው የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ቁጣ በእነዚህ ሰዎች ላይ እጅግ የነደደው፡፡ ከዚህ በኋላ ጅራፍ አበጅቶ ይሻሻጡና ይለዋወጡ የነበሩትን ሰዎችና የሚሸጡትን በሬዎች፣ በጎችና ርግቦች እየገረፈ ከቤቱ ካስወጣ በኋላ የለዋጮችን ገበታዎች ገለባብጦባቸዋል፤ የሚለዋወጡባቸውን ገንዘቦችም በታትኖባቸዋል፡፡ ይህን ከማድረጉ በፊት ግን «የአባቴን ቤት የንግድ ቤት አታድርጉት፡፡» በማለት ጥብቅ ማሳሰቢያ ሰጥቶአቸዋል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በከፍተኛ ቅንዓት ይህን ሁሉ ነገር ሲያከናውን አብረውት የነበሩት ደቀ መዛሙርቱ ያሰላስሉና ያስቡ  የነበረው አባታቸው ቅዱስ ዳዊት ስለ ጌታችን ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ቅንዓት በትንቢት መነጽር የተመለከተው ትንቢት መፈጸሙን ነበር፡-  «. . . ቤትህ ቅንዓት ይበላኛል፤» (መዝ 68፡9) የሚለው፡፡ ከዚህ በኋላ እነዚህ እኩያን አይሁድ ያደረገውን ነገር በምን ሥልጣን እንደሚያደርግ ይህን ለማድረጉም ምን ዐይነት ምልክት ሊሰጣቸው እንደሚችል ሲጠይቁት «ይህን ቤተ መቅደስ አፍርሱት፤ በሦስት ቀንም አፈርሰዋለሁ . . .» (ዮሐ 2፡19) በማለት ለእነርሱ ያልገባቸውን ነገር ስለ ገዛ ራሱ ሞትና ስለ ትንሣኤው በቤተ መቅደሱ መስሎ ነግሯቸዋል፡፡ ይህን አባባሉንም አብረውት የነበሩት ሐዋርያቱ ጌታ ከሙታን መካከል ከተነሣ በኋላ በመጽሐፍ የተጻፈውንና ኢየሱስ ክርስቶስ ያደረገውን ነገር በማሰብ በእርሱ አምነዋል፡፡ አይሁድ ግን ያደረጉት ክፉ ሥራ ሳያንሳቸው ለምልክት ጥየቃ ተመልሰው ወደ እርሱ በመምጣታቸው ለጥፋት ተዳርገዋል፡፡

አንድም ቤተ መቅደስ ተብሎ የተጠራው ይህ የእኛ ሰውነት ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ይህን ሁኔታ በመልእክቱ መላልሶና አስረግጦ ገልጦታል፡- «የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ እንደ ሆናችሁ፤ የእግዚአብሔርም መንፈስ እንዲኖርባችሁ አታውቁምን? ማንም የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ ቢያፈርስ እግዚአብሔር እርሱን ያፈርሰዋል፤ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ቅዱስ ነውና፤ ያውም እናንተ ናችሁ፡፡» 1ኛ ቆሮ. 3፥16-17፤1ኛ ቆሮ. 6፥19-20፡፡ ሰው የራሱ ሳይሆን የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ነው፤ በእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ውስጥ የሚኖረውና ሊኖር የሚገባው ደግሞ እግዚአብሔር ነው፡፡ እግዚአብሔር በቤተ መቅደሱ ውስጥ የሚኖረውም እኛን በከበረ ደሙ ፈሳሽነት ወይም በዋጋ ስለ ገዛንና መልሶ የራሱ ስላደረገን ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ከፈጠራቸው ፍጥረታት ሁሉ በላይ እኛን በመልኩና በምሳሌው የፈጠረን በእኛ ውስጥ ስለሚያድርና እኛን ቤተ መቅደሱ ስላደረገን ነው፡፡ ይህ በመሆኑም  እኛም ይህን አክበሮ፣ ባርኮና ቀድሶ የሰጠንን ቤተ መቅደስ ያለ ምንም ዕድፈትና ቆሻሻ በቅድስናና በንጽሕና ልንጠብቀው ይገባናል፡፡ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ አይሁድ እንዳደረጉት በከብቶች አዛባና ሽንት ሊቆሽሽ አይገባውም፡፡ አዛባና ሽንት የተባለው ኀጢአትና በደል ነው፡፡ ዝሙት፣ ርኩሰት፣ መዳራት፣ ጣዖት ማምለክ፣ ምዋርት፣ ጥል፣ ክርክር፣ ቅንዓት፣ ቁጣ፣ አድመኝነት፣ ክፋት፣ ተንኮል፣ ምቀኝነት. . . ወዘተ የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ ይኸውም እኛን የሚያቆሽሽ አዛባ ነው፡፡

እግዚአብሔር ደግሞ በቆሸሸ ቤት ውስጥ አይኖርም፡፡ የምንኖርበት ምድራዊ ቤት በተለያዩ ምክንያቶች ሲቆሽሽ ደስ እንደማይለን ሁሉ እኛም የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ (ራሳችንን) ስናቆሽሽ እግዚአብሔርን እንደማናስደስተው በማወቅ በንስሓ ልናጸዳው ይገባናል፡፡ እኛ ይህን ሰውነታችንን ወይም ይህን የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ በተለያዩ የኀጢአት ዐይነቶች የምናፈርሰው ከሆነ እግዚአብሔር ደግሞ አፍራሾቹን እኛን ያፈርሰናል፡፡ ዛሬ ብዙዎች የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ ወይም ሰውነታቸውን በተለያዩ ክፉ ቅጠሎች ማለትም በትንምባሆ፣ በሺሻና በጫት እያፈረሱት ነው፡፡ ከልክ ባለፈ መጠጥና በዝሙትም እያፈረሱት ነው፡፡ በሀሜትና በአሉባልታም እያፈረሱት ነው፡፡ በሐሰትና በስርቆትም እያፈረሱት ነው፡፡ እጅግ ብዙ የሚታገሥ እግዚአብሔር ደግሞ በንስሓ ካልተመለሱ እነርሱን አንድ ቀን ያፈርሳቸዋል፡፡ እርሱ ዛሬ ለአይሁድ ያነሳውን የገመድ ጅራፍ በእኛ ላይ በድጋሚ ለማንሣት ድጋሚ ይወለድ ዘንድ አይመጣም፤ በፍርድ ቀን በእሳት ጅራፍ ለመግረፍ እንጂ፡፡

አንዳንድ ጊዜ ብዙዎች የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስን በተለያየ ምክንያት ሲያፈርሱ ለሚመለከት ሰው መምህራችን ቅዱስ ጳውሎስ «ሥጋችሁ ከእግዚአብሔር የተቀበላችሁት በእናንተ የሚኖረው የመንፈስ ቅዱስ ቤተ መቅደስ እንደ ሆነ አታውቁምን?» (1ኛ ቆሮ 6፡19) በማለት በጻፈው የተግሣፅ ቃል ላይ በተመስጦ እንዲቆይ ያደርገውና በሰዎች አለማወቅ እንዲያዝንም ሆነ እንዲያለቅስ  ያደርገዋል፡፡ «አታውቁምን?» የሚለው ቃል የእኛን አለማወቅ ያጎላብኛል፡፡ ይኸው ሐዋርያ «አውቀውስ ቢሆኑ የክብርን ጌታ ባልሰቀሉትም ነበር፤. . .» (1ኛ ቆሮ 2፡8) በማለት ተናግሯል፡፡ ይህ ኀይለ ቃል ለአይሁድ ብቻ የተነገረ የሚመስለን ከሆነ ዛሬም እኛ አላወቅንም ማለት ነው፡፡ እነርሱ መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን የሰቀሉት አንድ ጊዜ ብቻ ነው፤ብዙዎቻችን ግን ኀጢአት በሠራን ቁጥር በሥራችን ብዙ ጊዜ መላልሰን እየሰቀልነው ነው፡፡ ብዙ ሰዎች ብዛት ያላቸው የኀጢአት ሥራዎችን ሲሠሩ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ የሆነ ሰውነታቸው እየሰቀሉትና እያፈረሱት መሆናቸውን በትክክል ቢያውቁ ኖሮ ከዚህ ክፉ ሥራቸው በታቀቡ ነበር፡፡ ባለማወቃቸው ግን የራሳቸውን፣ የሌሎችንና የእግዚአብሔርን አብያተ መቅደሰ እያፈረሱ ነው፤ በማፍረሳቸውም እግዚአብሔር እነርሱን እያፈረሳቸው ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን የምንታነጽ እንጂ የምንፈርስ ከመሆን ያድነን፡፡ የአምላካችን የእግዚአብሔር ፍቅር፣ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ እና የመንፈስ ቅዱስ ኅብረት ከእኛ ጋር ይሁን፤አሜን፡፡

ይቆየን፡፡

በጎውን ሁሉ ለእኛ ያደረገና የሚያደርግ እግዚአብሔር ስሙ የተመሰገነ ይሁን፤አሜን፡፡

ዓለም አቀፍ ሙቀትን በመከላከል ረገድ የገዳማትና አድባራት ብዝኀ ሕይወት እንክብካቤ ይሻል

የካቲት 22/2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደጀኔ

የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን በዓለም አቀፍ ደረጃ የሙቀት መጨመርን ለመቀነስ ያሏት ብዝኀ ሕይወት አስተዋጽኦቸው ከፍተኛ መሆኑን በማኅበረ ቅዱሳን ሙያ አገልግሎትና አቅም ማጎልበቻ ዋና ክፍል ሓላፊ ዶ/ር ሳሙኤል ኀይለ ማርያም አስታወቁ፡፡

ሓላፊው እንደገለጹት ማኅበረ ቅዱሳን በእቅድ ሊሠራቸው ካቀዳቸው መካከል የብዝኀ ሕይወት ጥበቃ  በታላቁ ደብረ ሊባኖስ ገዳም  እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በርካታ ገዳማትና አድባራት ያሏት መሆኑን የገለጹት ዶ/ር ሳሙኤል የደብረ ሊባኖስ ገዳምን ለጥናት መመረጡ ለጥናቱ መከናወን አመቺነት ካለው የቦታ ቅርበትና ከገዳሙ የብዝኀ ሕይወት ይዘትና ጥራት አንጻር መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን በደብረ ሊባኖስ ገዳም በጀመረው በዚህ ጥናት ላይ የግብርና ባለሞያዎች፣ የግብርና ምጣኔ ሀብት ባለሙያዎች፣ የአካባቢ ጥበቃ ባለሞያዎች እና በካርበን ልቀት ዙሪያ ልምድና ምርምር ያደርጉ ባለሞያዎች ያሉት ቡድን አቋቁሟል፡፡ ቡድኑ ከገዳሙ አመራር አካላትና ከማኅበረ ቅዱሳን ፍቼ ማእከል ጋር በመሆን ጥናቱን እያከናወነ መሆኑን ዶ/ር ሳሙኤል ጠቅሰው በጥናቱ ውጤትም ላይ መሠረት ያደረገ  ፕሮጀክት በገዳሙ ላይ የሚተገበር መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ጥናቱም የገዳሙን የብዝኀ ሕይወት ያለበትን ደረጃ  እንዲሁም በብዝኀ ሕይወቱ ላይ ተጽዕኖ የሚያደርሱትን ነገሮች መለየት፣ የዚህ ጥናት በመነሣት በቀጣይ መሠራት የሚገባቸውን ጉዳዮች ጭምር መሠረት ያደረገ እንደሚሆን ይጠበቃል፡፡

የደብረ ሊባኖስ ገዳም የብዝኀ ሕይወት ጥናት ቡድን ፕሮጀክቱን ሲተገብር የገዳሙ የአካባቢ ልማት እቅድ የሚወጣለት ሲሆን በገዳሙ ያሉት ብዝኀ ሕይወት ያለባቸው ቦታዎች ተለይተው ልዩ እንክብካቤ የሚደረግላቸው ይሆናል፡፡ የገዳሙም አኗኗር ብዝኀ ሕይወቱን ከመጠበቅ አንጻር መሆኑን ነው የተገለጸው፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ለብዝኀ ሕይወት ጥበቃ ከመቼውም በላይ ከሚመለከታቸው የዘርፉ ባለሞያዎችና መንግሥታዊና መንግሥታዊ ካልሆኑ አካላት ጋር በጥምረት ይሠራል ያሉት ዶ/ር ሳሙኤል ገልጸው ተፈጥሮአዊ ነገሮችን መንከባከብም ሆነ መጠበቅ ሃይማኖታዊ ግዴታም መሆኑን ነው የገለጹት፡፡

የብዝኀ ሕይወት ጥናት በአሁን ወቅት በዓለም አቀፍ ደረጃ ከፍተኛ ትኩረት እያገኘ ሲሆን በዓለማችን በየጊዜው በሚፈጠረው የሙቀት መጠን መጨመር ምክንያት ዓለማችንን አስጊ ደረጃ እያደረሳት ይገኛል፡፡

ምሁራን ለቤተ ክርስቲያን ቤተ ክርስቲያን ለሙህራን›› በሚል የጥናትና ምርምር ምሁራን የምክክር መርሐ ግብር ይደረጋል

የካቲት 22/2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደጀኔ

በማኅበረ ቅዱሳን የጥናትና ምርምር ማእከል ከጥናትና ምርምር ማእከል ባለሙያ ምሑራን ጋር የምክክር መድረክ መርሐ ግብር እንደሚያካሔድ አስታወቀ፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን የጥናትና ምርምር ዳሬክተርና በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የአርኪዮሎጂና ቅርስ አስተዳደር መምህር የሆኑት ዲ/ን መንግሥቱ ጎበዜ እንደገለጹት ምሁራን ለቤተ ክርስቲያን ቤተ ክርስቲያን፤ ለምሑራን ያላቸውን ተወራራሽ ጠቀሜታ በማጉላት፣ የምሑራንንም ፋይዳ ከቤተ ክርስቲያን ያገኙትንም ለመግለጽ ዐቢይ መርሐ ግብር መሆኑ ገልጸዋል፡፡ ይህ የውይይት መድረክ ለጥናትና ምርምር ማእከሉ አገልግሎቱን አጠናክሮ ለመቀጠል፣ የሌሎች ምሁራንን ድጋፍ ለማግኘትና ምሑራንም የቤተ ክርስቲያንን አገልግሎት እንዲያግዙ ለማነቃቃት ያግዛል፡፡ ምሑራኑም የጥናት ጽሑፎቻቸውን በቤተ ክርስቲያን ዙሪያ እንዲያደርጉ ከማገዝም በላይ ቤተ ክርስቲያንም ትልቅ የመረጃ ምንጭ በመሆን ለጥናታቸው ውጤታማነት ፋይዳዋ ታላቅ መሆኑን የሚረዱበት ይሆናል ብለዋል፡፡

በዚህ የጥናትና ምርምር ባለሙያዎች መርሐ ግብር ላይ የዘርፉ ባለሞያዎች የሚገኙ ሲሆን መርሐ ግብሩም በአዲስ አበባ ኢንተርኮንቲኔንታል ሆቴል የካቲት 23 ቀን 2004 ዓ.ም እንደሚካሔድ ገልጸዋል፡፡

በተያያዘ ዜና የጥናትና ምርምር ማእከሉ የካቲት 24 ቀን 2004 ዓ.ም በብሔራዊ ሙዚየም “የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን፣ ሀገርና የሀገር ሉዓላዊነት” በሚል ርዕስ ጥናት እንደሚቀርብ ገልጻôል፡፡ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ለአድዋ ድል መገኘት የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ድርሻ በመሆኑ በዓሉን ጥናታዊ ጽሑፍ እየቀረበ በየዓመቱ እንዲከበር በተሳታፊዎች የተሰጠ ጥቆማ ስለነበር የአድዋ ድል በዓልን ምክንያት በማድረግና ለሀገር አጠቃላይ የቤተ ክርስቲያን ሚና ማጉላት ዓላማ ያለው መሆኑ ተገልጿል፡፡

ቅዳሜ የካቲት 24 ቀን 2004 ዓ.ም ከቀኑ 7፡30 ጀምሮ በብሔራዊ ሙዚየም የሚቀርበው “የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን፣ ሀገርና የሀገር ሉዓላዊነት” ርዕስ በዋናነት የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የሀገርን ሉዓላዊነት በመጠበቅ አንጻር ምእመኗን አስተባብራ ድል ያስገኘች መሆኗ እና የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ከባሕል ወረራ ሀገርን የመከላከል ያላት አስተዋጽኦ ለማስገንዘብ የሚያስችል መሆኑን ዳይሬክተሩ ገልጸው በብሔራዊ ሙዚየም በሚደረገው መርሐ ግብር ሁላችሁም ተጋብዛችኋል በማለት መልእክት አስተላልፈዋል፡፡

asebot

ሰበር ዜና

የካቲት 21/2004 ዓ.ም.

በዲ/ን አብርሃም አንዳርጌ

የጥንታዊው አሰቦት ገዳም ደን ዳግም የእሳት አደጋ ቃጠሎ ደረሰበት፡፡

asebot

የአሰቦት ደብረ ወገግ ቅድስት ሥላሴና አባ ሳሙኤል ገዳም ደን ትላንት የካቲት 20 ቀን 2004 ዓ.ም. ባልታወቀ ምክንያት በተነሣ እሳት ቃጠሎ ደረሰበት፡፡

ትላንት ከቀኑ 5፡00 ሰዓት የተነሣው እሳት እስከአሁን ድረስ ያልጠፋ መሆኑንን የገለጹት የገዳሙ አገልጋይ አባ ወልዴ እንዳሉት እሳቱ እየተስፋፋ ከደኑ አልፎ ወደ ቅድስት ሥላሴ የአባቶች ገዳም እየተቃረበ መሆኑንን ገልጸዋል፡፡

እሳቱን ለማጥፋት የአካባቢው ገበሬ ማኅበር ጥረት እያደረገ ቢሆንም ከውኃ እጥረትና ከሰው ኀይል ማነስ የተነሣ ይህ ዜና እስከ ተጠናቀረበት ጊዜ ድረስ እሳቱ አለመጥፋቱን ለማወቅ ተችሏል፡፡

 

ዝርዝርሩን እንደደረሰን እናሳውቃለን፡፡

Derej A5

የመባዕ ሳምንት

Derej A5

abune abusade

ብፁዕ አቡነ አብሳዲ አረፉ

የካቲት 13/2004 ዓ.ም

በእንዳለ ደምስስ

abune abusadeብፁዕ አቡነ አብሳዲ በተወለዱ በ92 ዓመታቸው ቅዳሜ የካቲት 10/2004 ዓ.ም. ለእሑድ አጥቢያ በቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ፡፡ ብፁዕነታቸው በትግራይ ክፍለ ሀገር ሽሬ በ1912 ዓ.ም ተወለዱ፡፡ በ1926 ዓ.ም ከሽሬ ወደ ኤርትራ በመሔድና ደብረ ማርያም ገዳም በመግባት የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት በመከታተል ዲቁናን ከብፁዕ አቡነ ይስሐቅ፣ ቅስናን ደግሞ ከአቡነ ማርቆስ ተቀብለዋል፡፡ በደብረ ማርያም ገዳም ውስጥ በቆዩባቸው ዐሥር ዓመታት ውስጥ ከአንድ መቶ በላይ ዲያቆናትንና ካህናትን በማስተማር አፍርተዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ አብሳዲ በ1943 ዓ.ም በሱዳን በኩል ወደ ኢየሩሳሌም በእግራቸው የሔዱ ሲሆን፤ በግብጽ ለሁለት ዓመታት ለመቆየት ችለዋል፡፡ ከ1959 ዓ.ም. ጀምሮ ከ60 ዓመታት በላይ በኢየሩሳሌም የኖሩ ሲሆን ጥር 30 ቀን 1983 ዓ.ም በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ በኤጲስ ቆጶስነት ከተሾሙት ጳጳሳት መካከል አንዱ ናቸው፡፡ በኤጲስ ቆጶስነት እንደተሾሙ በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ገዳማት ሊቀ ጳጳስ ረዳት ኤጲስ ቆጶስ ሆነው እስከ ዕለተ እረፍታቸው ድረስ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በማገልገል ላይ ይገኙ ነበር፡፡

በቆይታቸውም በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ይዞታ የሆኑትን አብያተ ክርስቲያናትና ገዳማትን ለማስከበር ከፍተኛ ጥረት ያደረጉና ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመሟገት የተጣለባቸውን ሓላፊነት በመወጣት ሰፊ ሥራ ሠርተዋል፡፡ ብፁዕ አቡነ አብሳዲ ዕብራይስጥንና አረብኛ ቋንቋዎችን አቀላጥፈው ይናገሩም ነበር፡፡

ከቡኢ ምድረ ከብድ የሚወስደው መንገድ አገልግሎት መስጠት ጀመረ

የካቲት 13/2004 ዓ.ም

በእንዳለ ደምስስ

በጉራጌ ሀገረ ስብከት የሶዶ ወረዳ ዋና ከተማ ከሆነችው ቡኢ ከተማ ጀምሮ ምድረ ከብድ አቡነ ገ/መንፈስ ቅዱስ ገዳም ድረስ የሚወስደው የ18 ኪ.ሜትር ጥርጊያ መንገድ በፌደራል መንገዶች ባለሥልጣን መሥሪያ ቤት ሙሉ ትብብር ሥራው ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት መጀመሩን የገዳሙ አበምኔት አባ አብርሃም ወ/ኢየሱስ ገለጹ፡፡

ከዚህ ቀደም ይኸው መንገድ በአካባቢው ምእመናን አማካይነት በእጅ ቁፋሮ፣ ድንጋይ በመሸከምና ከጉልበት እስከ ገንዘብ አስተዋጽዖ በማድረግ አገልግሎት በመስጠት ላይ ነበር፡፡ ነገር ግን ከጊዜ ብዛት በመበላሸቱ በመኪናም ሆነ በእግር ወደ ገዳሙ ለመሔድ እጅግ አስቸጋሪ ሆኖ ቆይቋል፡፡ በዚህም ምክንያት ወደ ገዳሙ ለክብረ በዓላትም ሆነ ለጉብኝት የሚመጡ ምእመናን በመቸገራቸው ከጊዜ ወደ ጊዜ ቁጥራቸው እየቀነሰ መጥቷል፡፡

 

ሙሉ ወጪውን በመሸፈን መንገዱን በጥሩ ሁኔታ ሠርቶ ያስረከበውን የፌዴራል መንገዶች ባልሥልጣንን በእግዚአብሔር ስም ያመሰገኑት አበምኔቱ በመንገዱ መበላሸት ምክንያት ተቋርጦ የነበረውን የምእመናንና የገዳሙን ግንኙነት ለማጠናከር ይረዳል ብለዋል፡፡

 

ቀደም ሲል ገዳሙ ሰፊ የእርሻ መሬት ርስት የነበረው በመሆኑ በገዳሙ ውስጥ የሚገኙ መነኮሳትና መነኮሳይያት እርሻ በማረስና ሰብሎችን በመዝራት የጓሮ አትክልቶችን በማልማት ይተዳደሩ እንደነበር የገዳሙ አበምኔት ተናግረው፤ በአሁኑ ወቅት ግን ገዳሙ በቂ የእርሻ መሬት የሌለው በመሆኑ መተዳደሪያ ያደረገው በዓመት ሁለት ጊዜያት ጥቅምት 5 እና መጋቢት 5 በጻድቁ አቡነ ገ/መንፈስ ቅዱስ ዓመታዊ ክብረ በዓላት ከሚመጡ ምእመናን ከሚለግሱት የገንዘብና መባ አስተዋጽኦ ብቻ እንደሆነ የገዳሙ አበምኔት ጨምረው ገልጸዋል፡፡ ገዳሙ የልማት ሥራዎችን በመሥራት ለማጠናከርና በውስጡ የሚኖሩት መነኮሳት በችግር ምክንያት እንዳይበተኑ እንዲሁም ጥንታዊነቱንና ታሪካዊነቱን ጠብቆ ለማቆየት ከምእመናን ብዙ እንደሚጠበቅና በክብረ በዓላትም ሆነ በማንኛውም ጊዜ ገዳሙ ያለበትን ሁኔታ መጥተው በማየት የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እንዲያደርጉ አሳስበዋል፡፡

 

ገዳሙ በንጉሥ ላሊበላ ዘመነ መንግሥት  በራሳቸው በጻድቁ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ የተመሠረተ ሲሆን በጾምና ጸሎት የተጋደሉበት እንዲሁም ያረፉበት እንደሆነ ይታወቃል፡፡

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

የቅድስት ቤተልሔም የመጻሕፍት ቤትና የጉባኤ ቤት ተመረቀ

የካቲት 12/2004 ዓ.ም.

በዲ/ን አብርሃም አንዳርጌ

{gallery count=1 width=275 height=225 counter=1 links=0 alignment=right animation=3000}Beteleheme{/gallery}በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ፕሮጀክት የተገነባው በደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት በታች ጋይንት ወረዳ የምትገኘው የድጓ ማስመስከሪያ ቅድስት ቤተልሔም ቤተ ክርስቲያን የመጻሕፍት ቤትና የጉባኤ ቤት ተመረቀ፡፡

የካቲት 4 ቀን 2004 ዓ.ም በደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በብፁዕ አቡነ እንድርያስ የተመረቀው ይኸው መጻሕፍት ቤትና ጉባኤ ቤት ሙሉ ወጪውን የላስ ቬጋስ ምእመናን በዋናነት መሸፈናቸው ታውቋል፡፡

 

ኅዳር 26 ቀን 2003 ዓ.ም. የመሠረት ድንጋይ ተጥሎ በአንድ ዓመት ውስጥ የተጠናቀቀውን ግንባታ አስመልክቶ ብፁዕ አቡነ እንድርያስ ሲናገሩ የአብነት ትምህርት ቤቶች ለቤተ ክርስቲያናችን ህልውና ከፍተኛ ጠቀሜታ ያላቸው ናቸው፡፡ በመሆኑም ማኅበረ ቅዱሳን በዚህ ረገድ እያደረገ ያለው አስተዋጽዖ ቀላል የሚባል አይደለም” በማለት አመስግነዋል፡፡

 

በዕለቱ አጠቃላይ የሥራ ሒደቱን ዝርዝር ሪፖርት ያቀረቡት የድጓ ምስክር መምህር የሆኑት ሊቀምሁራን ይትባረክ ካሳዬ እንዳሉት “በግንባታው ምክንያት በተፈቀደልን ቦታ ላይ ፕሮጀክት ተቀርጾ የደብሩ ማኅበረ ካህናት፣ የድጓ አድራሾቹ ሁላችን ልማት እያለማን እራሳችንን የምንችልበት መንገድ ይፈልግልን፤ እስከ አሁን ለጉባኤ ቤታችን ለተደረገልን ሁሉ ማኅበረ ቅዱሳንን በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስም እናመሰግናለን” ብለዋል፡፡

 

በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት የቅስቀሳና ገቢ አሰባሳቢ ክፍል ሓላፊ ዲያቆን ደረጀ ግርማ በበኩሉ ማኅበሩ በቀጣይም ከቅድስት ቤተልሔም የድጓ ማስመስከሪያ ጎን በመሆን በጋራ ችግሮቹን በመፍታት እንደሚሠራ ጠቁሞ የገንዘብ ድጋፍ ያደረጉ የላስቬጋስ ምእመናንንና የአካባባውን ማኅበረሰብ ስለቀና ትብብራቸው አመስግኗል፡፡

 

በዕለቱም በድጓ ያስመሰከሩ የተወሰኑ አድራሾችና በግንባታው በጎ እንቅስቃሴ የነበራቸው ምእመናን ከብፁዕ አቡነ እንድርያስ እጅ የምስክር ወረቀት ተቀብለዋል፡፡ በቅድስት ቤተልሔም የድጓ ማስመስከሪያ በሀገራችን ብቸኛው ማስመስከሪያ መሆኑ ይታወሳል፡፡

ኢየሩሳሌም መታሰቢያ ድርጅት 49ኛ ዓመት የምስረታ በዓሉን አከበረ፡፡

የካቲት 9/2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደጀኔ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ምእመናን መታሰቢያ ድርጅት ለኢየሩሳሌም የካቲት 4 ቀን 2004ዓ.ም የተመሠረተበት 49ኛ ዓመት በዓል   ለድርጅቱን መሥራች ክብር አቶ መኮንን ዘውዴ  የመታሰቢያ ሐውልት ቦሌ ሩዋንዳ በሚገኘው መሰብሰቢያ አዳራሽ በር ላይ በማቆም ጭምር ተከብሯል፡፡

በ1955 ዓ.ም. ሚያዝያ 3 ቀን ከሠላሳ በማይበልጡ ኢትዮጵያውያን ወገኖች እንደተመሠረተ የሚነገረው መታሰቢያ ድርጅቱ በክብር አቶ መኮንን ዘውዴ ጠንሳሽነትና አሰባሳቢነት እንደሆነ ይነገራል፡፡ በወቅቱ ቅዱሳን መካናትን ለመሳለም ወደ ቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም የሔደው የምእመናን ቡድን በዚያ ያለውን ችግርና በገዳማቱ የሚኖሩ አባቶችና እናቶችን በደልና ስቃይ ተመልክቶ የነበረ ሲሆን በተለይ የዴር ሱልጣን ገዳማችን ወደ ጥንቱ ይዞታ ለመመለስ ካልተቻለበት ምክንያቶች አንዱ ከኢትዮጵያ ገዳማውያንን ለመጎብኘት የሚመጣ ሰው የለም የሚል ምክንያት እንደሚሰጥ መረዳታቸው ለድርጅቱ መመሥረት ምክንያት እንደሆነ ተገልጿል፡፡

ክብረ በዓሉን በንግግር የከፈቱት የድርጅቱ ምክትል ሊቀመንበር ኮሎኔል ተፈራ ይገዙ “የድርጅታችን የተመሠረተበትን 49ኛ ዓመት በምናከብርበትና በተልይም የታሪኩ ባለቤት ለሆኑት ክቡር አቶ መኮንን ዘውዴ የተሠራውን የመታሰቢያ ሐውልት በሚመረቅበት በዚህ ዕለት የተሰማንን ከፍተኛ መንፈሳዊ ደስታ ስንገልጽ ኩራት ይሰማናል” ብለዋል፡፡ “ሰው ለታሪክ የተፈጠረ እንጂ ታሪክ ለሰው አልተፈጠረም ያሉት ምክትል ሊቀ መንበሩ በ1955 ዓ.ም በኢየሩሳሌም ገዳማት የሚደርሰው በደል አሳዛኝ ታሪክ መነሻነት በብሔራዊና በመንፈሳዊ ስሜት በመቆርቆር ከብዙ ጥረትና ድካም በኋላ በርካታ አባላትን በማሰበሳብና የገዳማችንን ታሪክ በማስረዳት ለዚህ የቀደሰ ዓላማ ድጋፍ ለመስጠት ቃል የገቡትን ሰዎች ይዘው የኢየሩሳሌምን መታሰቢያ ድረጅትን የመሠረት ድንጋይ ሚያዝያ 16 ቀን 1956 ዓ.ም ያስቀመጡ የመጀመሪያው ታላቅ ሰው ከመሆናቸውም በላይ የድርጅቱን ዓላማ በተግባር በማዋል ከምንም አንስተው አሁን ያለበት ደረጃ እንዲደርስና በዓለም አቀፍ ደረጃም እውቅና እንዲያገኝ ያደረጉ ታላቅ አባት ናቸው” ብለዋል፡፡

 

ክቡር አቶ መኮንን ዘውዴ በተለይ የዴርስልጣን ገዳማችንን በተመለከተ ከፍተኛ ትኩረት በመስጠት ተቃዋሚ ወገኖች አጋጣሚ እየጠበቁ ሁከትና ውዝግብ በሚፈጥሩበት ወቅት ፈጥኖ በመድረስና በየቀጠሮም ቀን ከገዳም አባቶች ጋር  በእስራኤልአገር ፍርድ ቤት በመገኘትና ከአባቶች ጎን በመቆም ከፍተኛ የሞራልና የገንዘብ እርዳታ በየጊዜው ለገዳሙ እንዲሰጥ በማድረግ የሀገርና የቤተክርስቲያን ባለውለታ መሆናቸው ተወስቷል፡፡

 

 

በመክፈቻው ንግግራቸው ምክትል ሊቀመንበሩ ኮሎኔል ተስፋዬ ድርጅቱ ያከናወናቸውን ዋና ዋና ተግባራት የገለፁ ሲሆን “በጋምቤላ ክልል የሚገኙ ወጣቶችን ለማስተማርና በመንፈሳዊ ሕይወት ለማደራጀት በቤተ ክርስቲያን የተነደፈውን እቅድ በመደገፍ የጎዳና ተዳዳሪዎችን ችግር ለማስወገድ መንግሥት በልማት እንዲሳተፉ ለሚያደርገው እንቅስቃሴ የ700,000 ብር ድጋፍ በመንግሥትና በህዝብ ከፍተኛ ትኩረት የተሰጠውን የሕዳሴ ግድብ ሥራ የግማሽ ሚሊዮን ብር ቦንድ ያለ ወለድ ግዥ በማድረግ  ድርጅቱ  በኢየሩሳሌም ብቻ ሳይወሰን በአገር ውስጥም ለታሪክና መንፈሳዊ ሥራዎች ድጋፍ በመስጠት ላይ ነው” ብለው በተለይ በተፈጥሮ አደጋ ሳቢያ ወላጆቻቸውን ያጡ ሕፃናትን አሰባስቦ በረጲ፣ በአለም ከተማ፣ በደብረ ብርሃን የሕፃናትን በማስተማርና በመንከባከብና በአሁኑ ወቅት ዘላቂነት ያለው ሥራ ለመሥራት የ800,000 ብር ፕሮጀክት በመቅረጽ ውጤታማ ተግባር ለማከናወን በመንቀሳቀስ ላይ ይገኛል” ብለዋል፡፡

በበዓሉ ላይ የተገኙት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ቀዳማዊ ርዕስ ሊቃነ ጳጳሳት ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ኘሬዝዳንት የዓለም ሃይማኖቶች ለሠላም የክብር ኘሬዝዳንት “ክቡር አቶ መኮንን ዘውዴን የማውቃቸው የትምህርት ሚኒስቴር በነበሩበት ወቅት ነው፤ ያስተማሩኝ፣  በአዳሪ ትምህርት ቤትም እንድንማር ያደረጉኝ ታላቅ ሰው ናቸው” ያሉት ቅዱስነታቸው ለትውልድ ታሪክንና ክብርን ላቆዩ ስሞች ክብር ይገባቸዋል ለእኝህ አባት መታሰቢያ ሐውልት እንዲያቆምላቸው ድርጅቱ መወሰኑና ታሪክን ለትውልድ እንዲቆይ በማድረጉ ሊመሰገን ይገባዋል፡፡ መልካምነታቸውን ለትውልድ ልናስተላልፍ ይገባናል) ድርጅቱም አገልግሎቱን አጠናክሮ በመላው ዓለም ጽ/ቤት ከፍቶ ሊሠራ ይገባል” ብለዋል፡፡

የክቡር አቶ መኮንን ዘውዴ የመታሰቢያ ሐውልት ምረቃ ላይ ቅዱስ ፓትሪያርኩን ጨምሮ ሊቃነ ጳጳሳት፣ የጥንታዊት ኢትዮጵያ ጀግኖች አርበኞች፣ የክቡር አቶ መኮንን ባለቤት ከነ ቤተሰቦቻቸው፣ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶችና የድርጅቱ አባላት ተገኝተዋል፡፡ በበዓሉ ላይም የቅዱስ ኡራኤል ሰንበት ትምህርት ቤት መዘምራን መዝሙር ያቀረቡ ሲሆን ቅድስት ሀገረ ኢየሩሳሌምን በማስመልከት ትምህርት ተሰጥቷል፡፡