debube omo 2 1

በደቡብ ኦሞ ከሰባት መቶ በላይ ሰዎች ተጠመቁ

ታኅሣሥ 1 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ


debube omo 2 1በማኅበረ ቅዱሳን የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ ፕሮግራም አስተባበሪነት፤ በደቡብ ኦሞ ሀገረ ስብከት ሥር የሚገኙና በልዩ ልዩ ቤተ እምነቶች ውስጥ የነበሩ ከሰባት መቶ በላይ ኢትዮጵያውያን ሥርዓተ ጥምቀት ተፈጽሞላቸው ወደ እናት ቤተ ክርስቲያን ተመለሱ፡፡ በሜጸር የቅዱስ ሚካኤል እንዲሁም በቶልታ የቅድስት ሥላሴ አብያተ ክርስቲያናት ውስጥ ኅዳር 23 ቀን 2005 ዓ.ም. በተከናወነው ሥርዓተ ጥምቀት ሀብተ ወልድና ስመ ክርስትና ያገኙ ሰዎች በማኅበረ ቅዱሳን የጂንካ ማእከልና በሰንበት ትምህርት ቤት ጥምረት በሁለት ልዩ ልዩ የስብከት ኬላዎች አማካኝነት ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ሲማሩ የቆዩ ናቸው፡፡

 

debube omo 2 2አዳዲስ ተጠማቂያኑ ለዝግጅት ክፍላችን በሰጡት አተያየት ፡ በተፈጸመላቸው ሥርዓት ጥምቀት እጅግ በጣም መደሰታቸውን ገልጸው፤ በአቅራቢያቸው ቤተ ክርስቲያን እንዲታነፅላቸው ጥያቄ አቅርበዋል፡፡ በጉዳዩ ላይ ያነጋገርናቸው ብፁዕ አቡነ ኤልያስ የደቡብ ኦሞ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል  “የምእመናኑ ጥያቄ ተገቢ ነው፡፡ አብያተ ክርስቲያናቱ ሲቋቋሙ አብሮ መተዳደሪቸውም ሊታሰብ ይገባዋል፤ በአንዳንድ ቦታዎች ላይ እንዳስተዋልነው ምእመናን በቅንነት በዚህ ቦታ እንዲህ ያለ ታቦት ይተከልልን እኛ ሙሉ ወጪውን እንሸፍናለን በማለት ያሳነፅዋቸው አብያተ ክርስቲያናት ምእመናኑ በሕይወት እስካሉ ድረስ ያገለግሏቸውና፤ እነሱ ከዚህ ዓለም በሞተ ሥጋ ሲለዩ አገልግሎቱ እየተቋረጠ አብያተ ክርስቲያናቱ እስከ መዘጋት የደረሱባቸው ሁኔታዎች አሉ፡፡ ስለሆነም ቤተ ክርስቲያኗ እንዴት ትገለገላለች? በሚለው ላይ ማኅበረ ቅዱሳንን ጨምሮ በመላው ዓለም የሚገኙ የቤተ ክርስቲኒቱ ልጆች ሊያስቡበት ይገባል፡፡ አብያተ ክርስቲያናትም ሁል ጊዜ በልመና መተዳደር የለባቸውም” ብለዋል፡፡

 

በማኅበረ ቅዱሳን ስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ ፕሮግራም፤ የፕሮግራሙ አስተባባሪ የሆኑት ሊቀ ብርሃናት ሃይማኖት ተስፋዬ ስለ ተከናወነው አገልግሎት ሲናገሩ “ስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ ፕሮግራሙ በዐስር ዓመታት ለመፈጸም ከያዛቸው ዕቅዶች አንዱ በጂንካ ማእከል አማካኝነት ለንዑሳን ክርስቲያኖች በአቅራቢያቸው የስብከት ኬላዎችን (ቃለ እግዚአብሔር የሚሰሙባቸው ቤቶች)  እንዲቋቋምላቸውና መሠረታዊ የሃማኖት ትምህርት እንዲያገኙ ማድረግ ነበር፡፡ ይህም በእግዚአብሔር ቸርነት የተፈጸመ ነው፡፡ በቅርቡም በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል መተከል ሀገረ ስብከት በማንዲራና ድብጤ ወረዳዎች ሲያስተምራቸው ለነበሩት ሰዎች በቅርቡ የማጥመቅ ተግባርን ለመፈጸም ዝግጅቱ ተጠናቋል” ብለዋል፡፡

 

debube omo 2 4የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያው በቶልታና ሜጠር ቀበሌዎች ላስጠመቃቸው አዳዲስ ምእመናን በቀጣይ ለሚፈጽምላቸው  እገዛ አስመልክተው ሊቀ ብርሃናት ሃማኖት ተስፋዬ እንዲህ ብለዋል፡፡ “የልጅነት ጥምቀት አግኝተው በቅርቡ ወደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ለገቡ ምእመናን በአቅራቢያቸው ሥርዓተ አምልኮ የሚፈጽሙባቸውን አብያተ ክርስቲያናትን ማነፅና እነሱንም ማጽናት ይጠበቅብናል፡፡”