ራሱን “ጉባኤ አርድእት ዘኦርቶዶክስ ተዋሕዶ” ብሎ የሚጠራውን ቡድን የቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት አገደ

ነሐሴ 9 ቀን 2004 ዓ.ም.

በዲ/ን አብርሃም አንዳርጌ

 

በጠቅላይ ቤተ ክህነት አካባቢ ራሱን “ጉባኤ አርድእት ዘኦርቶዶክስ ተዋሕዶ” ብሎ የሰየመውን ቡድን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት የእገዳ ደብዳቤ ጣለበት፡፡

 

የቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት የጉባኤው ዓላማና ፍላጎት ምን እንደሆነ እንደማይታወቅና እንዲህ ዓይነቱ ጉባኤ በቅዱስ ሲኖደስ ካለመቋቋሙም በላይ እውቅና ሳያገኝና ሳይፈቀድለት በራሱ ተነሳሽነት የሚንቀሳቀስ በመሆኑ የቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤትም የማያውቀውና ተቀባይነት የሌለው በመሆኑ በቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት ዋና ጸሓፊና የከፋ ሸካ ቤንች እና ማጂ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል ፊርማ ለመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት በቁጥር 486/836/2004 ሐምሌ 25 ቀን 2004 ዓ.ም. በተጻፈው ደብዳቤ መታገዱ ተገልጿል፡፡

 

“ጉባኤ አርድእት ዘኦርቶዶክስ ተዋሕዶ” በማለት ስለ ተቋቋመው ቡድን ያነጋገርናቸው የጠቅላይ ቤተ ክህነት አንዳንድ የመምሪያ ሓላፊዎች ቡድኑ በምን ምክንያት እንደተቋቋመና ለምንስ በኅቡዕ መንቀሳቀስ እንደፈለገ እንዳልተረዱ ጠቅሰው ጉዳዩን ለቤተ ክርስቲያኗ ደኅንነት ሲባል በአንክሮ እየተከታተሉ እንደሚገኙ ተናግረው በቤተ ክርስቲያኒቱ መዋቅር ውስጥ ሆነው የዚህን ሕገ ወጥ ቡድን አባላት በሆኑ ግለሰቦች ላይ ቀኖናዊና አስተዳደራዊ ርምጃዎች በቀጣይ እንደሚወስድም የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ምንጮች ገልጸውልናል፡፡

 

ጉባኤውን እያደራጁ የሚገኙ ግለሰቦች አብዛኛዎቹ በሚሠሩባቸው ቦታዎች ተቀባይነት እያጡ የመጡ ግለሰቦች እንደሆኑ የሚናገሩት የቤተ ክህነቱ ምንጮች ቅዱስ ሲኖዶስ እነዚህ ግለሰቦች ሊፈጥሩት ካሰቡት ከፍተኛ አደጋ ቤተ ክርስቲያኒቱን ሊታደጋት እንደሚገባ አመልክተዋል፡፡

 

የዚህ የእገዳ ደብዳቤ ግልባጭ ለብፁዕ ወቅዱስ ፓትሪያርክ ልዩ ጽ/ቤት፣ ለፌደራል ጉዳዮች ሚኒስቴር ለሃይማኖትና ሥነ ሥርዐት ዳይሬክቶሬት ጀኔራል፣ ለብሔራዊ ደኅንነትና መረጃ አገልግሎት፣ እንዲሁም ለፌደራል ፖሊስ ኮምሽን እና ለአዲስ አበባ ፖሊስ ኮምሽን ግልባጭ የተደረገ መሆኑን ለመረዳት ችለናል፡፡

 

picture1

የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ የ2004 ዓ.ም. እቅዶቹን በማጠናቀቅ ላይ እንደሚገኝ ገለጸ፡፡

ነሐሴ 8 ቀን 2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

 

በማኅበረ ቅዱሳን ትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ መርሐ ግብር በ2004 ዓ.ም. ሊያከናውናቸው ካቀዳቸው የአገልግሎት ዘፍፎች በአብዛኛው እያጠናቀቀ መሆኑን ገለጸ፡፡

 

የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ መርሐ ግብር ክፍል ሓላፊ የሆኑት ሊቀ ብርሃናት ሃይማኖት ተስፋዬ 2004 ዓ.ም. የክፍሉ የአገልግሎት አፈጻጸም አስመልክቶ እንደገለጹት “በታቀደው መሠረት በመላው ሀገሪቱ 200 የሕዝብ ጉባኤያትን 15 ሐዋርያዊ ጉዞዎችን ለማድረግ ታስቦ ሙሉ ለሙሉ ተግባራዊ ተደርገዋል፡፡ እንዲሁም በ10 ሀገረ ስብከቶች ውስጥ ለሚገኙ ካህናት የትምህርተ ኖሎትና የአስተዳደር የአሠልጣኞች ሥልጠና ለመስጠት ታስቦ በ8ቱ ሀገረ ስብከቶች ተተግብረዋል፡፡ በ10 ሀገረ ስብከቶች ውስጥ ለሚገኙ ሰንበት ትምህርት ቤቶች የተተኪ መምህራን ሥልጠና በታሰበው መንገድ ተሰጥቷል፡፡ ሰልጣኞቹም በየሀገረ ስብከታቸው በመንቀሳቀስ እያንዳንዱ ሀገረ ስብከት ሠላሳ ሠላሳ ሌሎች ሰልጣኞችን እንዲያሰለጥኑ በመደረግ ላይ ሲሆን ነሐሴ 16 ቀን 2004 ዓ.ም. ይጠናቀቃል ተብሎ ይጠበቃል” ብለዋል፡፡

 

የሰለጠኑት ካህናትና የሰንበት ትምህርት ቤት አባላት ወደታች ወርደው ሥልጠናውን ሲሰጡ ለመገምገም መቻሉን የገለጹት ሊቀ ብርሃናት ሃይማኖት ተስፋዬ “ሥልጠናው የካህናትና የተተኪ መምህራን ብቃት የሚያጎለብት እንደሆነ ጨምረው የገለጹ ሲሆን ሰንበት ትምህርት ቤቶች ያልተቋቋመባቸው ቦታዎች ላይ በማቋቋም የማጠናከሪያ አገልግሎት በመስጠት ወደተግባር መሸጋገራቸውን በተደረገወ ግምገማ ለማረጋገጥ መቻሉን ጨምረው ገልጸዋል፡፡

 

በ2005 ዓ.ም. ይህ አገልግሎት ተጠናክሮ የሚቀጥል ሲሆን የክፍሉ ሓላፊ ሊቀ ብርሃናትት ሃይማኖት ተስፋዬ ማኅበረ ቅዱሳን በግቢ ጉባኤያት ያሰለጠናቸው አቅም ያላቸው ተማሪዎችና ከመንፈሳዊ ኮሌጆች ትምህርታቸውን በመከታተል ላይ የሚገኙና የተመረቁ መምህራን ወደየመጡበት ሀገረ ስብከት በክረምቱ ስለሚሄዱ ሥልጠናዎችንና የስብከት አገልግሎት እንዲሰጡ በቅንጅት እየተከናወነ እንደሚገኝ አስታውቀዋል፡፡

 

ስላጋጠማቸው ችግር ሲገልጹም “ከፍተኛ ችግራችን የገንዘብና የመገልገያ ቁሳቁስ እጥረት ነው፡፡ በ2004 ዓ.ም. 10 የስብከት 10 የመዝሙር ካሴቶችንና በ4 የተለያዩ ቋንቋዎች መጻሕፍት ተዘጋጅተዋል፡፡ በኦሮምኛና በሲዳምኛ መዝሙር በኦሮምኛና በአማርኛ መጻሕፍት ተዘጋጅተዋል፡፡ እነዚህን ለምእመናን ለማዳረስ መታተም አለባቸው፡፡ ነገር ግን ዝግጅቶቹ ቢጠናቀቁም በገንዘብ እጥረት ምክንያት ሊሳካልን ባለመቻሉ በእጃችን ይገኛሉ፡፡ እነዚህንና ሌሎችም የስብከተ ወንጌል አገልግሎትን ለማስፋፋት እንድንችል ከ35 ሚሊዮን ብር በላይ ያስፈልገናል፡፡ ይህንንም ከበጎ አድራጊ ምእመናን እንጠብቃለን፡፡ በተጨማሪም የቢሮ መገልገያ ቁሳቁስ የተጠቀሙበትና የቀየሩት ኮምፒውተር፣ ፕሪንተርና ሌሎችም ድጋፍ ያደረጉ የገጠር ቤተ ክርስቲያናትን፣ የወረዳና ሀገረ ስብከቶችን ለማጠናከር ጠቀሜታ ስላላቸው ከምእመናን ብዙ ይጠበቃል በማለት ሊቀ ብርሃናት ሃይማኖት ተስፋዬ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡

ሀገረ ስብከቱ የ2004 ዓ.ም. ዕቅድ አፈጻጸምን ገምግሞ የአዲስ ዓመት ዕቅድን አጸደቀ፡፡

ነሐሴ 3 ቀን 2004 ዓ.ም.

ከጅማ ማእከል

  • ቅዱስ ሲኖዶስ ሕግ አውጥቶ ያዋቀረውን ማኅበር በአክራሪነት መፈረጅ ቤተ ክርስቲያንን መፈረጅ ነው፡፡

የጅማ ሀገረ ስብከት ጠቅላላ ጉባኤ የ2004 ዓ.ም. ዕቅድና ክንውንን በመገምገም፣ የ2004 ዓ.ም. ዕቅድን በማውጣትና መመሪያ በመቀበል ሰኔ 28-29 ቀን 2004 ዓ.ም. ተካሂዶ ተጠናቀቀ፡፡

 

ጉባኤውን የመሩት የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ ጠቅላላ ጉባኤው የ2004 ዓ.ም. የሥራ ግምገማ ማድረጉ ካለፈው ተሞክሮ በመውሰድ ለቀጣይ የተሻለ ለመሥራትና የቤተ ክርስቲያንን አገልግሎት ለማሻሻል የሚረዳ በመሆኑ በቀጣይም የተሳካ ሥራን ለመሥራት ሁሉም የበኩሉን እንዲወጣ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡

 

የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ መልአከ ብርሃን ስለሺ አስፋው ከ2004 ዓ.ም. የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት በተጨማሪ ሀገረ ስብከቱ የተዘጉ አብያተ ክርስቲያናትን ለማስከፈት ይረዳ ዘንድ እየተሠራ ያለው ባለ 5 ፎቅ ሕንፃ ግንባታን በተመለከተ የሒሳብ ራፖርት አቅርበዋል፡፡ ለዚህ ሥራም ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያበረከቱ አድባራትና ግለሰቦችን አመሰግነዋል፡፡

 

በጉባኤው ማጠቃለያ ላይም ብፁዕነታቸው ባስተላለፉት መልእክት በአንዳንድ ግለሰቦችና ድርጅቶች ቅዱስ ሲኖዶስ ሕግ አውጥቶ ያዋቀረውን ማኅበረ ቅዱሳንን በአክራሪነት ስም መፈረጅ ቤተ ክርስቲያንን መጥቀስ በመሆኑ ይህን የሚያደርጉ አንዳንድ አካላት ከድርጊታቸው መታረም እንዳለባቸው አሳስበዋል፡፡

 

በመጨረሻም በሀገረ ስብከቱ በበጀት ዓመቱ ብልጫ ሥራ የሠሩ አካላት የተሸለሙ ሲሆን የማኅበረ ቅዱሳን የጅማ ማእከል የዓመቱ ልዩ ተሸላሚ መሆኑን ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡

 

በሀገረ ስብከቱ በዘንድሮው ዓመት ከሁለት መቶ በላይ የሚሆኑ ወገኖች ከተለያዩ ቤተ እምነቶች ወደ ኦርቶዶክሰ ተዋሕኦ ሃይማኖት እንደተመለሰም በሪፖርቱ ተካቷል፡፡ የ2005 ዓ.ም. ጠቅላላ ጉባኤን በአጋሮ ከተማ እንዲዘጋጅ በመወሰን ጉባኤው ተጠናቋል፡፡

 

ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 19ኛ ዓመት ቁጥር 22 ከነሐሴ 1-15 ቀን 2004 ዓ.ም.

ማኅበረ ቅዱሳን የ20 ዓመት ጉዞውን ሊገመግም ነው፡፡

ነሐሴ 1 ቀን 2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደጀኔ

ከ1984 ዓ.ም. ጀምሮ መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት እየሰጠ ያለው ማኅበረ ቅዱሳን ያሳለፋቸውን ሁለት ዐሥርት ዓመታት ጉዞውን የሚገመግም መሆኑ ተገለጸ፡፡

 

yseraamerare 005የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ ሊቀ ትጉኀን ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ሥዩም በነሐሴ ወር የሚደረገውን የማኅበሩን ጠቅላላ ጉባኤ አስመልክተው እንደገለጹት ማኅበረ ቅዱሳን ያከናወናቸው የ20 ዓመት ጉዞዎች በጠቅላላ ጉባኤው ላይ አንሥቶ እንደሚገመግም ገልጸዋል፡፡

 

ከ1986 ዓ.ም. ጀምሮ በየ2 ዓመት ጠቅላላ ጉባኤ ማድረግ መጀመሩን የገለጹት ሰብሳቢው ማኅበረ ቅዱሳን 20ኛ ዓመት የምሥረታ በዓሉን በሚያከብርበት ወቅት የሚካሄደው ጠቅላላ ጉባኤ ታሪካዊ ነው ብለዋል፡፡ ከነሐሴ 26-28 ቀን 2004 ዓ.ም. ለ3 ቀናት በሚዘልቀው ጉባኤ ቁጥራቸው ከአንድ ሺህ በላይ የሚሆኑ ተሳታፊዎች የሚገኙበት ሲሆን በዚህም ጉባኤ ከሀገር ውስጥና ከውጪ ማእከላት፣ ወረዳ ማእከላትና ግቢ ጉባኤያት የሚሳተፉበት እንዲሁም ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ ተጋባዥ እንግዶች የሚገኙበት መሆኑን አስታውቀዋል፡፡

 

ለ3 ቀናት በሚካሄደው 10ኛ ጠቅላላ ጉባኤ ቀጣይ የ4 ዓመት ስልታዊ እቅድ ከማጽደቅ ጀምሮ ቀጣዩን የአመራር ምርጫም እንደሚያደርግ ይጠበቃል፡፡

 

ለ10ኛ ጊዜ በሚደረገው ጠቅላላ ጉባኤ ከሀገር ውስጥ 44 ማእከላት፣ ከውጪ 9 ማእከላትና ግንኙነት ጣቢያዎች፣ 303 ወረዳ ማእከላት፣ እንዲሁም የግቢ ጉባኤያት ተወካዮች እንደሚገኙና ተጋባዥ እንግዶችን ጨምሮ ከአንደ ሺህ በላይ ተሳታፊዎች በጉባኤው ላይ ይታደማሉ፡፡

የማኅበራዊ አገልግሎትና ልማት ክፍሉ ለአረጋውያን እርዳታ አደረገ፡፡

ሐምሌ 24 ቀን 2004 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ


በማኅበረ ቅዱሳን የአዲስ አበባ ማእከል የማኅበራዊ አገልግሎትና ልማት ክፍል ባሳለፍነው ሳምንት ረጅም ዘመናትን በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ውስጥ ላሳለፉ አረጋውያን ጊዜያዊ የአልባሳትና የሕክምና እርዳታ አደረገ፡፡

የአገልግሎት ክፍሉ አብዛኛውን የእድሜ ዘመናቸውን በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ላይ አድርገው ለኖሩ ሰባት አባቶች የአልባሳት እገዛ dsc01699ያደረገው በ2004 ዓ.ም. መሪ እቅዱ መሠረት መሆኑን የጠቀሱት የክፍሉ ሓላፊ ወይዘሪት መቅደስ ዓለሙ፤ “ይህንን ለማቀድ ምክንያት የሆነን አባቶቻችን ከሰፊ የአገልግሎት ዘመናቸው በኋላ የሚታሰብላቸው የጡረታ አበል አለመኖሩ ነው፡፡ አብዛኛዎቹ አባቶችም በቅርብ የሚረዳቸውና የሚንከባከባቸው ሰው የሌላቸው ናቸው፡፡ ስለሆነም ምንም ዓይነት አገልግሎት እንዳልሰጡ በቂ ትኩረት ተነፍጓቸውና ተረስተው በየመቃብር ቤቱና ንጽሕና በተጓደለባቸው ሥፍራዎች ወድቀው የሚገኙትን አባቶች፤ ከሰንበት ትምህርት ቤቶች ጋር በመተባበር ባካሄድነው ጥናትና ባገኘነው መረጃ መሠረት መርጠን ረድተናል፡፡” በማለት ምክንያቱን አስረድተዋል፡፡

የማኅበራዊ አገልግሎትና ልማት ክፍሉ በልዩ ልዩ ቦታዎች ለሚገኙ አረጋውያን ካበረከተው የአልባሳት አስተዋጽኦ በተጨማሪ በበጎ አድራጊdsc01709 ምእመን ቤት ተጠግተው ለሚኖሩ አንድ አባት ሙሉ የሕክምና ወጪ በመሸፈን እንዲታከሙ አድርጓአል፡፡

 

በስተመጨረሻም ወይዘሪት መቅደስ ዓለሙ “ከጊዜያዊ እርዳታ ባለፈ በቀጣይ አረጋውያኑን ለማቋቋምና ኑሮአቸውን ለማሻሻል በክፍሉ ምን ታስቧል?” በሚል ለቀረበላቸው ጥያቄ “እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ይህ እቅድ በ2005 ዓ.ም. ተጠናክሮ የሚቀጥል ይሆናል፡፡ ክፍሉም እንደ ክፍል በአቅም ከፍ ይላል ብለን እናስባለን፡፡ እናም በቀጣዩ ዓመት ከጊዜያዊ እርዳታ ይልቅ የተሻለ እገዛ ማበርከት የምንችልበትን ዝግጅት አጠናቅቀናል፤ ጊዜው ሲደርስም ይህንኑ እንፈጽማለን ብለን ተስፋ እናደርጋለን፡፡” ብለዋል፡፡

 

በተያያዘ ዜና የአገልግሎት ክፍሉ በበኪ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን የአብነት ትምህርት ቤት ለሚገኙ ተማሪዎች ማቋቋሚያ የሚሆን ፕሮጀክት ነድፎ እየሠራ መሆኑን በተለይ  ለመካነ ድራችን በሰጠው መግለጫ አስረድቷል፡፡ ከዚህ ቀደም  በአገልግሎት ክፍሉ አማካኝነት ለተማሪዎች ጊዜያዊ የአልባሳትና የቀለብ እገዛ የተደረገ ሲሆን፤ በዚህ ዓመት ግን ተግባራዊ የሆነውና  በሦስት ሔክታር መሬት ላይ  ያርፈው የእርሻ ሥራ ሙሉ ለሙሉ የተማሪዎችን ችግር ይቀርፋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

 

dsc01744በሦስት ሔክታር መሬት ላይ ጤፍ ለመዝራት አስፈላጊውን ቅድመ ዝግጅት መደረጉን ያወሱት የአገልግሎት ክፍሉ ኃላፊ ወይዘሪት መቅደስ “መሬቱን በትራክተር ከታረሰበት ከመጀመሪያው ቀን አንስቶ ለሦስት ተከታታይ ጊዜያት የአከባቢው ገበሬዎች አርባ ጥማድ በሬዎቹን ይዘው እንዲሁም፤  ምእመናን በገንዘባቸውና በጉልበታቸው  አማካኝነት ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክተዋል፡፡ … ከደብሩ አስተዳደር ጀምሮ ሌሎችም መደበኛ  አገልጋዮችና ምእመናን ለቤተ ክርስቲያን ሁለንተናዊ እድገት በጋራ እንሥራ የሚለውን መርሕ የተቀበሉ ናቸው፡፡ ይህም በሌሎች ቦታዎች ለሚገኙ የቤተ ክርስቲያን አካላት መልካም ተሞክሮ ነው፡፡” በማለት በማጠቃለያ መልእክታቸው በፕሮጀክቱ ትግበራ ላይ የተባበሩትን ሁሉ አመስግነዋል፡፡

በዝቋላ ገዳም የወተት ላም እርባታ ፕሮጀክት ተግባራዊ ሊደረግ ነው፡፡

ሐምሌ 24 ቀን 2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስ


ለዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም የወተት ላም እርባታ ፕሮጀክት ለመተግበር ስምምነት ላይ መደረሱ ተገለጸ፡፡

 

በገዳሙ በቅርቡ ከፍተኛ የደን ቃጠሎ ተከስቶ እንደነበር የሚታወስ ሲሆን ገዳሙን ለመርዳት በሀገር ውስጥና በመላው ዓለም የሚገኙ ምእመናን የገንዘብና የቁሳቁስ ድጋፍ በማድረግ ላይ እንደሆኑ ይታወቃል፡፡ በዚህም መሠረት ማኅበረ ቅዱሳን ምእመናንን በማስተባበር ከ600,000.00 ብር /ስድስት መቶ ሺህ ብር/ በላይ ለማሰባሰብ መቻሉን የማኅበሩ ዋና ጸሓፊ ዲ/ን ሙሉጌታ ኃይለ ማርያም ገልጸዋል፡፡ ከዚህ ገንዘብ ውስጥ አብዛኛው በማኅበረ ቅዱሳን የአሜሪካ ማእከል አስተባባሪነት በአሜሪካ የሚገኙ የማኅበረ በዓለወልድ እና የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት ያሰባሰቡት መሆኑ ታውቋል፡፡

የተገኘውን እርደታ ወደ ተግባር ለመለወጥ በታቀደው መሠረት “ለገዳሙ ቋሚ ፕሮጀክት እንደሚያስፈልገው ስለታመነበት ቦታው ድረስ ባሙያዎች በመላክ የዳሰሳ ጥት የተደረገ ሲሆን ከገዳሙ ሓላፊዎች ጋር ውይይት ተደርጓል፡፡ በውይይቱም ለገዳሙ ትልቅ ጥቅም የሚሰጠው የትራክተር ግዢ ቢሆንም ለጊዜው የተሰበሰበው ገንዘብ ይህንን ለማስፈጸም የማይበቃ በመሆኑ ከዚህ በፊት ተጀምሮ የነበረው የወተት ላም እርባታ ፕሮጀክት እንዲተገበር ስምምነት ላይ ተደርሷል” በማለት የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጸሓፊ ዲ/ን ሙሉጌታ ኃይለ ማርያም ገልጸዋል፡፡ በስምምነቱ መሠረት የማኅበሩ የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ፕሮጀክቱን እንደሚያስፈጽም ተናግረዋል፡፡

 

የገዳሙ ደን በተቃጠለበት ወቅት የቀለብ እጥረት በመከሰቱ ማኅበሩ ምእመናንን በማስተባበር 50 ኩንታል ስንዴ 20 ኩንታል ጤፍ፣ 40 ሺህ ብር የሚገመት መጠጥ ውኃ፣ በሶ፣ ስኳር፣ ዳቦ ድጋፍ ማድረጉን መዘገባችን ይታወሳል፡፡

ቅዱስ ሲኖዶስ ስለ ማኅበረ ቅዱሳን የወሰነው ውሳኔ ለማኅበሩ መድረሱ ተገለጸ

ሐምሌ 23ቀን 2004 ዓ.ም

በእንዳለ ደምስስ


የ2004 ዓ.ም. የግንቦቱ ርክበ ካህናት የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ስለ ማኅበረ ቅዱሳን የወሰነው ውሳኔ   በደብዳቤ የተገለጸ መሆኑን የማኅበሩ ጽ/ቤት አስታወቀ፡፡ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፤ የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ፕሬዚዳንት፤ የዓለም ሃይማኖቶች ምክር ቤት ለሰላም የክብር ፕሬዚዳንት ለብፁዕ አቡነ ፊልጶስ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ የኢሉባቦርና ጋምቤላ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በጻፉት ደብዳቤ ማኅበሩ ለብፁዕነታቸው ተጠሪ እንዲሆን በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ መወሰኑን ጠቅሰው ከማኅበሩ እድገት ጋር አብሮ ሊሄድ እንዲችል የማኅበሩ መተዳደሪያ ደንብ አስጠንተው ለጥቅምት ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ እንዲያቀርቡ አሳስበዋል፡፡

 

ቅዱስነታቸው በቁጥር 451/275/2004 በቀን 13/11/2004 ዓ.ም. በጻፉት ደብዳቤ “ማኅበረ ቅዱሳን ከሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ተለይቶ የራሱ የሆነ መተዳደሪያ ደንብ ተጠንቶ እስኪወጣለት ድረስ ተጠሪነቱ ለብፁዕነትዎ ሆኖ ሲሠራ እንዲቆይ በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ ተወስኗል፡፡” በማለት ያስታወሱት ቅዱስ ፓትርያርኩ መተዳደሪያ ደንቡን እንዲያጠኑ በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ የተመረጡትን የብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ስም ዝርዝር ጠቅሰዋል፡፡በዚህም መሠረት ብፁዕ አቡነ ገብርኤል የሲዳማ፤ ጌዴኦና አማሮ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤ ብፁዕ አቡነ ገሪማ የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽ/ቤት የውጭ ግንኙነት የበላይ ሓላፊ ፤የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ፕሬዚዳንትና የዓለም ሃይማኖቶች ምክር ቤት የክብር ፕሬዚዳንት ቢሮ ዋና ጸሐፊና የድሬዳዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤ ብፁዕ አቡነ ያሬድ የሰበካ ጉባኤ ማደራጃ መምሪያ ሊቀ ጳጳስ የሰዋሰወ ብርሃን መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ሓላፊ፤ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ የከምባታ ሐድያና ጉራጌ አህጉረ ስብከት እና የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሊቀ ጳጳስ፤ ከሕግ ባለሙያዎችና ከማኅበረ ቅዱሳን አባላት ጋር በመሆን መተዳደሪያ ደንቡን አስጠንተው ለጥቅምት ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ እንዲያቀርቡ ገልጸዋል፡፡

 

ማኅበረ ቅዱሳን ከሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ወጥቶ ለጠቅላይ  ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ  ተጠሪ እንዲሆን  በግንቦቱ ርክበ ካህናት የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የተወሰነ ሲሆን በዚሁ ወቅት ቅዱስ ሲኖዶስ ስለማኅበሩ በሰጠው አስተያየት “ማኅበረ ቅዱሳን የመሥራት አቅሙ ከፍተኛ ደረጃ ላይ የደረሰና በቤተ ክርስቲያኒቱ እየሠራ ባለው ሥራ ሁሉ አብተ ክርስቲያናትንና ገዳማትን በስፋት እየጠቀመ ያለ በምሁራን የታቀፈ፤ ሁለንተናዊ ዝግጅት ያለው ማኅበር ስለሆነና ብዙ የልማት ሥራዎችን በመሥራት ላይ የሚገኝ በመሆኑ እራሱን የቻለ ድርጅታዊ መዋቅር ሊዘረጋለት ይገባል” ማለቱ ይታወሳል፡፡

“ዝክረ ቅዱስ ቂርቆስ” በሚል መሪ ቃል የተዘጋጀው መንፈሳዊ መርሐ ግብር ተጠናቀቀ፡፡


ሐምሌ 17 ቀን 2004 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ

1በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የሚገኘው የደብረ ምሕረት ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ትምህርት ቤት ያዘጋጀው መርሐ ግብር ከሐምሌ 12 እስከ ሐምሌ 15 ቀን ተካሄደ፡፡ ዝግጅቱ በሁለት ዐበይት ክፍሎች ተከፍሎ የተካሄደ ሲሆን፡- ይህም ከመክፈቻው ሐምሌ 12-14 በዐውደ ርዕይ፣ እንዲሁም ሐምሌ 15 ቀን 12 ሰንበት ትምህርት ቤቶች የተሳተፉበት መንፈሳዊ መርሐ ግብር የቀረበበት መሆኑ ታውቋል፡፡

 

ለ3 ቀናት የቆየውን ዐውደ ርዕይ በጸሎት የከፈቱት የደብረ ምሕረት ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን  አስተዳዳሪ መልአከ ገነት አባ ኀይለ ማርያም መንገሻ  ዐውደ ርዕዩን በጸሎት ከከፈቱ በኋላ በሰጡት አስተያየት በዕድሜ ሕፃናት የሆኑት ልጆች ባዘጋጁት መርሐ ግብር ከፍተኛ ደስታና ኩራት እንደተሰማቸው ገልጸው፡- “የዛሬ አበባ የነገ ፍሬ የሆኑ ሕፃናት ልጆቻችንን በደንብ ልንንከባከባቸው ይገባናል፡፡ ይህንንም ካደረግን በመጪው ጊዜ ቤተ ክርስቲያንን የሚረከብ ትውልድ በብዛት ብቻ ሳይሆን በጥራትም እናፈራለን፤ ይህም ታላቅ ተስፋችን ነው፡፡” ብለዋል፡፡ መልአከ ገነት አባ ኀይለ ማርያም በማጠቃለያ መልእክታቸው “የአድባራት አስተዳዳሪዎችን ጨምሮ በየአጥቢያ ቤተ ክርስቲያን የምንገኝ መሪጌቶችና አገልጋዮች በሙሉ ለሰንበት ትምህርት ቤት አስፈላጊውን ድጋፍ ማድረግ አለብን፡፡ ይህ ካልሆነ ግን የነገዋን ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ፈተና ውስጥ እንደሚገባ ልንረዳ ይገባናል” ብለዋል፡፡

 

5“ሰንበት ትምህርት ቤታችን ከዚህ ቀደም የተለያዩ ዐውደ ርዕዮችን ያዘጋጀ ሲሆን ሕፃናትን በተመለከተ ግን ይህ ዐውደ ርዕይ የመጀመሪያው ነው፡፡ ሕፃናትን የተመለከተ ዐውደ ርዕይ እንድናቀርብ የተፈለገበት ዋነኛው ምክንያት ተገቢውን ትኩረት ለሕፃናት እንዲሰጥ ለመቀስቀስ ነው፡፡” በማለት ዐውደ ርዕዩ በሕፃናት ዙሪያ እንዲከናወን ምክንያት ስለሆነው ሁኔታ ያስረዳው ወጣት ዮሐንስ መረቀኝ የደብረ ምሕረት ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ትምህርት ቤት ምክትል ሰብሳቢ ነው፡፡

 

“በቀደምት ኢትዮጵያውያን ወላጆቻችን ዘንድ እንደ ልምድ ተይዞ የነበረው ልጆችን በሕፃንነት እድሜአቸው ወደ አብነት ትምህርት ቤት የመላክ ሁኔታ አሁን አሁን እየተቀየረ÷ በዘመናዊ ትምህርት ብቻ እንዲማሩ ማድረግ  ‘ባሕል’ እየሆነ የመጣበት ጊዜ ላይ በደረስንበት በዚህ ወቅት ሕፃናት ሥርዐተ ቤተ ክርስቲያንን፣ ትምህርተ ሃይማኖትን፣ ጸሎቱንና የመሳሰለውን እንዲማሩና እንዲያውቁ የማስቻል ሓላፊነት ሰንበት ትምህርት ቤቶችና ወላጆች ልንወጣ ይገባናል፡፡በዐውደ ርዕዩ ላይ የተካተቱት ልዩ ልዩ ክፍሎች ሕፃናት በቤተ ክርስቲያን ያላቸውን ተስፋ ለማመላከት ታስበው የተዘጋጁ ናቸው” በማለት ወጣት ዮሐንስ አስረድቷል፡፡

 

25 የሚደርሱ ሕፃናት በገላጭነት የተሳተፉበት ዐውደ ርዕዩ በ8 ልዩ ልዩ ክፍሎች ተከፋፍሎ የተዘጋጀ ሲሆን በዋነኝነት ሕጻናት ሊቃውንት፣ ሕጻናት ሰማዕታት፣ ሕጻናት በመጽሐፍ ቅዱስ፣ ሕጻናትና ሥራዎቻቸው ፣ ሕጻናትና ጥፋታቸው፣ እንዲሁም ለወላጆች የሚሉና መሰል ሌሎች ክፍሎች የተካተቱበት ነበር፡፡

 

በመዝጊያ መርሐ ግብሩ ላይ በደብረ ምሕረት ቅዱስ ሚካኤል ሰንበት ትምህርት ቤት አማካኝነት “ቁጥሮች ለሕፃናት” እንዲሁም 12ቱም ሰንበት ትምህርት ቤቶች በጋራ የተሳተፉበት “ድምፀ ሕፃናት” በሚል ርዕስ የተዘጋጁ የኅትመት ውጤቶች ተመርቀው ለአንባብያን ቀርበዋል፡፡

አውሮፓ ማእከል ጠቅላላ ጉባኤውን አካሄደ

ሐምሌ 13 ቀን 2004 ዓ.ም.

በዲ/ን ዶ/ር መርሻ አለኸኝ


  • የማኅበረ ቅዱሳን 20ኛ ዓመት እና የአውሮፓ ማእከል 12ኛ ዓመት ምሥረታ በዓል በስውድን ተከበረ።

በማኅበረ ቅዱሳን የአውሮፓ ማእከል ጠቅላላ ጉባኤውን ከሰኔ 29 እስከ ሐምሌ 1 ቀን 2004 ዓ.ም. በሀገረ ስዊድን ስቶክሆልም ከተማ አካሄደ። ከመላው አውሮፓ የተሰባሰቡ ec_membersየማኅበሩ አባላት፣ በስዊድን የተለያዩ ከተሞች የሚያገለግሉ ካህናትና ምእመናን በተሳተፉበት በዚህ ጠቅላላ ጉባኤ የማእከሉ የ2004 ዓ.ም. የአገልግሎት ሪፖርት ቀርቦ ውይይት ተደርጎበታል። በውይይቱም ማእከሉ በአገልግሎት ዘመኑ አጠናክሮ የሰጣቸውን አገልግሎቶች በቀጣዩ ዓመትም አጠናክሮ እንዲቀጥልባቸው ሊፈጽማቸው ያቀዳቸው ነገር ግን በልዩ ልዩ ምክንያት መፈጸም ያልቻላቸውን ወይም ከታቀደው በታች ያከናወናቸውን አገልግሎቶች በሚቀጥለው ዓመት እንዲፈጽማቸው ውሳኔ አሳልፏል።

 

ማኅበረ ቅዱሳን በኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ በተለይም በሬድዮ እየሰጠ ያለውን ሰፊ አገልግሎት ለመደገፍ ማእከሉ ባቋቋመው የሬድዮ ቤተሰብ አማካይነት እያደረገ ስላለው ድጋፍና ቀጣይ ሂደትም ተወያይቶ ጠቃሚ ውሳኔዎችን አሳልፏል። ከዚህም ጋር በዋናው ማእከል እየተተገበረ ያለው የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ ፕሮጀክት በታቀደለት ጊዜና ዝርዝር ተግባራት መሠረት ይፈጽም ዘንድ ማእከሉ ባቋቋመው የድጋፍ ሰጪ አስተባባሪ ቡድን አማካይነት በመስጠት ላይ ስላለው ድጋፍ ሪፖርት ቀርቦ ጉባኤው ሰፊ ውይይት በማድረግ ልዩ ልዩ የማሻሻያ ውሳኔዎችን አሳልፏል።

 

ጉባኤው ማኀበረ ቅዱሳን በቅዱሳት መካናትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ድጋፍ ገዳማት ከሚያመርቷቸው ምርቶች የአውሮፓmk_eu_12th_anniversary ምእመናን ተጠቃሚ በሚሆኑበት ሁኔታ ላይም ተወያይቶ ውሳኔዎችን በማሳለፍ ለተፈጻሚነታቸው በማእከሉ ስር ላለው ቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ክፍል ከባድ ኃላፊነት ሰጥቷል። የጉባኤውን ከፍተኛ ትኩረት አግኝቶ ሰፊ ውይይት የተደረገበት ሌላው አጀንዳ “የአውሮፓ ማእከል አባላት የአገልግሎት ሱታፌ ከማኀበረ ቅዱሳን ተልእኮ አንጻር” በሚል ርእስ የቀረበው ጥናት ነበር። በማእከሉ ሥራ አስፈጻሚ ጉባኤ በተቋቋመው ቡድን ተዘጋጅቶ የቀረበው ይህ ጥናት በሁሉም የአውሮፓ ሀገራት የሚገኙ አባላት በቤተ ክርስቲያን መዋቅር ሥር ታቅፈው በመስጠት ላይ ያሉትን አገልግሎት የዳሰሰ፣ ጥንካሬዎችንና ድክመቶችን ነቅሶ ያወጣ፣ ወደፊት ሊደረግ የሚገባውን ያመላከተ ሰፊ ጥናት ነበር። ጉባኤው በጥናቱ ላይ ሰፊና ሞቅ ያለ ውይይት አድርጎ ውሳኔዎችን አሳልፏል።

 

ጉባኤው ከዋናው ማእከል የተላከለትን ሪፖርትና መልእክት በተወካዩ አማካይነት በማድመጥ ውይይት አድርጓል። ጉባኤው የማኀበራችንን 20ኛ ዓመት እንዲሁም የአውሮፓ ማዕከልን 12ኛ ዓመት የምሥረታ በዓል ማእከሉ በተመሠረተበት ሀገር በስዊድን በደመቀ ሁኔታ አክብሯል።

 

ga_2004_participantsበመጨረሻም ጉባኤው በቀረበለት የቀጣዩ የ2005 ዓ.ም. የአገልግሎት ዘመን ዕቅድ ላይ ተወያይቶ የማሻሻያ ዐሳቦችን በመስጠት ካጸደቀ በኋላ ማእከሉን ለቀጣዮቹ ሁለት ዓመታት የሚመራ አዲስ የሥራ አስፈጻሚ ጉባኤ መርጦ የጉባኤው ፍጻሜ ሆኗል። ማእከሉ ስምንት የግንኙነት ጣቢያዎች እና አምስት ቀጠና ማእከላት ያሉት ሲሆን በስዊድን ቀጠና ማእከል የተዘጋጀው የዘንድሮው ጉባኤ የተሳካ እንደነበር የጉባኤው ተሳታፊዎች አስተያየታቸውን ሰጥተዋል። ቀጠና ማእከሉ ለጉባኤው መሳካት አስተዋጽዖ ያደረጉትን አባላትና ምእመናን እንዲሁም ተቋማት በተለይ ጉባኤው በተመቼ ሁኔታ ይካሄድ ዘንድ መሰብሰቢያ አዳራሽና የተሳታፊዎችን ማረፊያ ቤት ከሙሉ አገልግሎት ጋር በነጻ የሰጠውን በብሬድንግ የስዊድን ቤተ ክርስቲያን አመስግኗል።

 

ረድኤተ እግዚአብሔር አይለየን።

ልዩ የሕፃናት መርሐ ግብር ተዘጋጀ

ሐምሌ 10 ቀን 2004 ዓ.ም.

በፍጹም ዓለማየሁ

hitsanat

በ12 የአዲስ አበባ ሰንበት ትምህርት ቤቶች የጋራ ጥምረት እና በአፍሪካ ኅብረት ደብረ ምሕረት ቅዱስ ሚካኤል ካቴድራል ሰንበት ትምህርት ቤት አዘጋጅነት ለሕፃናት የሚሆን መርሐ ግብር ተዘጋጅቷል፡፡ መርሐ ግብሩ ከሐምሌ 12-15/2004 ዓ.ም. ለአራት ቀናት የሚካሄድ ሲሆን በሦስቱ የመጀመሪያ ቀናት “ዝክረ ቅዱሳን ሕፃናት በልሣነ ሕፃናት” በሚል መሪ ቃል በአስተናጋጅ ሰንበት ትምህርት ቤት ሕፃናት የተዘጋጀ ዐውደ ርዕይ ይቀርባል፡፡ ከመርሐ ግብሩ አስተባባሪዎች እንደተረዳነው ሐሙስ ሐምሌ 12 ከጠዋቱ 3፡00 ሰዓት የሚከፈተው ይህ ዐውደ ርዕይ የሕፃናቱን የእደ ጥበብ ውጤቶች ጨምሮ 8 ክፍሎች ይኖሩታል፡፡

በተጨማሪም በመርሐ ግብሩ ማጠናቀቂያ ሐምሌ 15 ዕለተ እሑድ ከቀኑ 6፡00 ጀምሮ በሚካሄደው “ዝክረ ቅዱስ ቂርቆስ ወሕፃናት” በተሰኘው የሕፃናት ጉባኤ፣ በመርሐ ግብሩ ተሳታፊ የሰንበት ትምህርት ቤቶች ሕፃናት የተዘጋጀ ወረብ፣ መንፈሳዊ ቅኔ፣ የኪነ ጥበብ ፍሬዎች በተጨማሪም በሕፃናቱ የተዘጋጀ ስለ ቅዱስ ቂርቆስ ተራኪ የሆነ ፊልም የሚቀርብ ሲሆን በሥዕል የተደገፈ የሕፃናት መጽሐፍ በዕለቱ ይመረቃል፡፡ በዕለቱም ቅዱሳን ሊቃነ ጳጳሳትና የደብር አስተዳዳሪዎች እንደሚገኙ ለማወቅ ተችሏል፡፡ በዕለቱም ሕፃናት ልጆችዎን ይዘው በመርሐ ግብሩ ላይ እንዲገኙ የመርሐ ግብሩ አስተባባሪዎች ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡