medere kebde

ማኅበረ ቅዱሳን በምድረ ከብድ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ አንድነት ገዳም ያስገነባቸው ፕሮጀክቶች ተመረቁ፡፡

ጥቅምት 8 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ


medere kebdeማኅበረ ቅዱሳን በጉራጌ ሀገረ ስብከት በምድረ ከብድ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ አንድነት ገዳም ሲያከናውናቸው የነበሩት የመጠጥ ውኃና የአብነት ትምህርት ቤት ግንባታ ፕሮጀክቶች ተጠናቀው ጥቅምት 4 ቀን 2005 ዓ.ም. በብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ የከምባታ፣ ሀድያ፣ ጉራጌና ስልጢ አህጉረ ስብከትና የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሊቀ ጳጳስ ተመረቁ፡፡

 

የምረቃ መርሐ ግብሩ ጸሎተ ወንጌል በማድረስ የተጀመረ ሲሆን 100 ሺህ ሊትር መያዝ የሚችለው የኮንክሪት የውኃ ማጠራቀሚያmedere kebde 1 በብፁዕነታቸው ተመርቋል፡፡ በተጨማሪም የአብነት ትምህርት ቤቱ በብፁዕነታቸው ተባርኮ የተመረቀ ሲሆን እያንዳንዱን ክፍል በመዘዋወር ጎብኝተዋል፡፡ በግንባታው የተካተቱት 12 የተማሪዎች ማደሪያ ክፍሎችና ሌሎች 4  ለመምህራን የተዘጋጁት ክፍሎች ሲሆኑ በእያንዳንዱ የተማሪዎች ማደሪያ ክፍል ባለ 2 ተደራራቢ አልጋዎች ይገኛሉ፡፡ 4 ለመምህራን የተዘጋጁት ክፍሎች በቅርቡ ሙሉ የመኝታ ቁሳቁስ እንደሚሟላላቸው ተገልጿል፡፡

 

ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ በሰጡት ቃለ ምዕዳን “በዚህ ታላቅ ገዳም በቅዱሳን አባቶቻችን በታሪካቸውና በገድላቸው እንዲሁም በቃል ኪዳናቸው አሻራ ላይ ነው ያለነው፡፡ የቅዱሳን በረከት ለኢትዮጵያ ሀገራችን ትልቅ ዋጋ አለው፡፡ ዓለም በመከራ ሲናጥ ኢትዮጵያ እግዚአብሔርን የያዙ ቅዱሳን ጸሎትና አፅማቸው ጠብቋታል፡፡ የጻድቁ አባታችን አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ በተጋድሎ ከፀኑበት ቦታ ላይ ነው የምንገኘው፡፡ ያኔ በዚህ ቦታ ላይ እነሱና መላእክት ብቻ ነበሩ የከተሙት፡፡ ምድራውያን ሰዎች ሰማያውያን መላእክት የሆኑበት ቦታ ነው፡፡ ዛሬ ደግሞ እኛ በዚህ አለም ስንኖር የቅዱሳኑን ፈለግ ተከትለን ለበረከት ነው የመጣነው፡፡ በዚህ ቦታ ተገኝታችሁ ይህንን ቅዱስ ገዳም ለመርዳትና ለመደገፍ የወጣችሁ፤ የወረዳችሁ ሁሉ ዋጋችሁ ታላቅ ነው፡፡” ብለዋል፡፡

 

medere kebde 4የምድረ ከብድ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ አንድነት ገዳም አበምኔት አባ አብርሃም ወልደ ኢየሱስም ማኅበረ ቅዱሳን ስላከናወነው ተግባር ሲገልጹ “ማኅበረ ቅዱሳን እያከናወነ ያለው አገልግሎት ለዓመታት ስንቸገርበት የነበረውን የውኃ ችግር የፈታ ነው፡፡ ለ6 ወራት ከብቶች በ3 ቀናት ልዩነት ነው ውኃ የሚያገኙት፡፡ እኛም የገዳሙ ማኅበረ መነኮሳት በሳምንት በነፍስ ወከፍ 10 ሊትር ውኃ ብቻ ነው የምናገኘው፡፡ ከዚህ በፊት ውኃ ለማምጣት እስከ 40 ደቂቃ ይወስድብን ነበር፡፡ ሄደንም ወረፋ ጠብቀን ነው የምናገኘው፡፡ አንዳንዴም ተሰልፈንም ላይሳካልን ይችላል፡፡ ዛሬ ማኅበረ ቅዱሳን ከ100 ሺህ ሊትር ውኃ የሚይዝ ማጠራቀሚያ ሠርቶልን ችግራችን ተወግዷል፡፡” በማለት በውኃ ችግር ምክንያት ያጋጠማቸውን ሁሉ መፍትሔ ማግኘቱን ተናግረዋል፡፡ በተጨማሪም የአብነት ትምህርት ቤቱን በማስመልከት 48 ተማሪዎች ተቀብሎ ማስተማር እንደሚያስችልና የግንባታ ወጪውን ገዳሙ በመሸፈን ማኅበረ ቅዱሳን 150 ቆርቆሮ፤ 24 አልጋ፤ 24 ፍራሽ፤ 48 ብርድ ልብስ፤ 48 አንሶላ፤ 48 ትራስ  ወጪውን በመቻል ለምረቃ እንደበቃ ገልጸዋል፡፡

 

በገዳሙ ውስጥ ከሚታዩ ከፍተኛ ችግሮች መካከል አንዱ የምግብ አቅርቦት እጥረት እንደሆነ የገለጹት የገዳሙ አበምኔት ለተማሪዎቹ የተያዘ በጀት ባለመኖሩ ማኅበረ መነኮሳቱ በየቀኑ ከሚሰጣቸው ዳቤ እየቆረሱ በማካፈል ላይ እንደሚገኙ አብራርተዋል፡፡ በገዳሙ ውስጥ 28 መነኮሳይት፤ 41 መነኮሳትና መናንያን ፤48 የአብነት ተማሪዎች እንደሚገኙና የምግብ ፍጆታቸውንም በየዓመቱ መጋቢት 5 ቀን በሚከበረው የጻድቁ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ የእረፍታቸው መታሰቢያ በዓል ቀን ለማክበር ከአዲስ አበባና ከተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች ከሚመጡ ምእመናንና በጎ አድራጊዎች ከሚለግሱት እንደሆነ አበምኔቱ ይናገራሉ፡፡

 

በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት የልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የቦርድ ሰብሳቢ ኢንጂነር ግዛቸው ሲሳይ ለምድረ ከብድmedere kebde 3 አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ አንድነት ገዳም ማኅበሩ ስላከናወነው ሥራ ባቀረቡት ሪፖርት “የውኃ ታንከር ሥራው በግንቦት ወር 2004 ዓ.ም. እንዲጠናቀቅ በማድረግ ውኃ መያዝ እንዲችል ተደርጓል፤፤ ግንባታው የተሠራው ከመሬት በላይ ሲሆን 100 ሺህ ሊትር ውኃ የመያዝ አቅም አለው፡፡ በገዳሙ አካባቢ ምንም የገጸ ምድርም ሆነ የከርሰ ምድር ውኃ ማግኘት አስቸጋሪ በመሆኑ ያለው ብቸኛ አማራጭ ከዝናብ የሚገኘውን ውኃ ከጣሪያ ላይ በመሰብሰብ /Roof Catchment/ ዘዴ በመጠቀም ነው፡፡ ይህ ፕሮጀክት በመሠራቱ ምክንያት ቢያንስ ለ50 መነኮሳት ለእያንዳንዳቸው በቀን እስከ 7 ሊትር ውኃ ዓመቱን ሙሉ እንዲያገኙ ያስችላል፡፡” በማለት ያብራሩ ሲሆን በውኃ እጦት ምክንያት ይሰደዱ የነበሩት መነኮሳትና መናንያን ቁጥር እንደሚቀንስና ወደ ገዳሙ የሚመጡ መናንያን ቁጥርም ሊጨምር እንደሚችል ተናግረዋል፡፡ ለውኃ ፕሮጀክቱም 493፣459.25 ብር እንደሚያስፈልገው  በእቅድ ተይዞ የነበረ ቢሆንም በ409፣572 ብር ወጪ ሊጠናቀቅ መቻሉንና ወጪውንም ከተለያዩ በጎ አድራጊ ምእመናን ፤ የድሬዳዋ የቀድሞ ተመራቂዎች የቅድስት ድንግል ማርያም ጽዋ ማኅበርና ከባንኮች የሠራተኛ ጉባኤ እንደተገኘ ጨምረው ገልጸዋል፡፡

 

ሁለተኛው ፐሮጀክት የአብነት ትምህርት ቤቱ ሲሆን 124፣466.10 ወጪ በማድረግ የቆርቆሮ፤ የአልጋ፤ የፍራሽ፤ የአንሶላና የትራስ ወጪዎችን መሸፈን እንደተቻለ በሪፖርታቸው ያመለከቱ ሲሆን ከፊል ወጪውን በማኅበረ ቅዱሳን የካናዳ ማእከል በኩል እንደተገኘ ማኅበሩ ለአንድ የአብነት መምህር በየወሩ 300 ብር ድጎማ እንደሚያደርግ ገልጸዋል፡፡ በአጠቃላይ ለሁለቱ ፕሮጀክቶች 534፣038.10 ብር ወጪ መሆኑንም በሪፖርታቸው አመልክተዋል፡፡

 

የተጠናቀቁትም ፕሮጀክቶች በማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጸሐፊ ዲ/ን ሙሉጌታ ኃ/ማርያምና በገዳሙ አበምኔት አባ አብርሃም ወልደ ኢየሱስ መካከል የፕሮጀክት ርክክብ ሥነ ሥርዓት ተካሂዷል፡፡ ለፕሮጀክቶቹ መጠናቀቅ ከፍተኛ ሚና ለነበራቸው ለገዳሙ አበምኔት ለአባ አብርሃም ወልደ ኢየሱስ የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ያዘጋጀላቸውን ስጦታ ያበረከተ ሲሆን አባ አብርሐምም ለቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍልና ፕሮጀክቱን በተገቢው ሁኔታ በመሥራት ላጠናቀቀው ተቋራጭ ልዩ ስጦታ አበርክተዋል፡፡

 

በመርሐ ግብሩ ላይ የማኅበረ ቅዱሳን ሥራ አመራርና ሥራ አስፈጻሚ አባላት፤ በጎ አድራጊ ምእመናን የተገኙ ሲሆን በዲያቆን ያረጋል አበጋዝ ትምህርተ ወንጌል፤ በማኅበሩ መዘምራን ያሬዳዊ ዝማሬ፤ እንዲሁም የቅኔ ዘረፋ በገዳሙ መምህር ቀርቧል፡፡ በመጨረሻም  በብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ የከምባታ፣ ሀድያ፣ ጉራጌና ስልጢ አህጉረ ስብከትና የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሊቀ ጳጳስ ቡራኬና ጸሎት ተጠናቋል፡፡

metshate 3

2ኛው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የጥናት መጽሔት ተመረቀ

ጥቅምት 8 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

metshate 3በማኅበረ ቅዱሳን የጥናትና ምርምር ማእከል የተዘጋጀው 2ኛው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የጥናት መጽሔት/Journal/ ጥቅምት 3 ቀን 2004 ዓ.ም. ከቀኑ 8፡00 ሰዓት ጀምሮ በኢንተር ኮንቲኔንታል ሆቴል ተመረቀ፡፡ በጥናት መጽሔቱ የምረቃ መርሐ ግብር ላይ ብፁዕ አቡነ ሉቃስ የሰቲት ዑመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤ በማኅበረ ቅዱሳን የጥናትና ምርምር ማእከል አማካሪ ቦርድ ሰብሳቢ፤ ብፁዕ አቡነ ኤልያስ የሰሜን ኦሞ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤ የጥናት መጽሔቱን በማዘጋጀት የተሳተፉ ምሁራን፤ ጥሪ የተደረገላቸው ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና ምሁራን የተገኙ ሲሆን በብፁዕ አቡነ ሉቃስ ቡራኬ በጸሎት ተከፍቷል፡፡

 

የእንኳን ደህና መጣችሁ መልእክት በማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጸሐፊ ዲያቆን ሙሉጌታ ኀይለ ማርያም የቀረበ ሲሆን በመልእክታቸውም “ማኅበረ ቅዱሳን የጥናትና ምርምር ማእከል ሲያቋቁም ቤተ ክርስቲያን ያለፈችበትን ፈርጀ ብዙ ተግዳሮቶች መንፈሳዊና ሳይንሳዊ በሆነ መንገድ አጥንቶ ትክክለኛ መፍትሔ ለመጠቆም፤ ርቀው ያሉትን  የቤተ ክርስቲያን ምሁራን ለማቅረብ፤ ወደ ቤተ ክርስቲያንም ቀርበው በሙያቸው እንዲያገለግሉ ለማድረግ ነው፡፡ ከዚህም ባሻገር ቤተ ክርስቲያን ቀመስ የሆነው የሀገሪቱ ሁለንተናዊ ሀብት በጥናትና ምርምር መሣሪያነት በመግለጽ፤ በመተንተንና በማሳተም ለዓለም ህዝብ ለማድረስ፤ በውጤቱም ቤተ ክርስቲያን የቁሳዊና መንፈሳዊ ግኝቶች ተጠቃሚ እንድትሆን ለማስቻል ነው፡፡” በማለት መልእክታቸውን ያስተላለፉ ሲሆን የዕለቱን  ጉባኤ በንግግር እንዲከፍቱ በማኅበረ ቅዱሳን የጥናትና ምርምር ማእከል አማካሪ ቦርድ ምክትል ሰብሳቢና በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የታሪክ ትምህርት ክፍል ኀላፊ የሆኑትን ዶክተር ውዱ ጣፈጠን ጋብዘዋል፡፡

 

ዶክተር ውዱ ጣፈጠ ባደረጉት ንግግር “ቤተ ክርስቲያናችን የፍልስፍና ፤ የሥነ ጽሁፍ፤ የሥነ ሕንፃ፤ የሥነ ሥዕል፤ የሥነ ሰብዕ፤ የሥነ ማኅበረሰብ፤ የአስተዳደርና የሥነ ትምህርት . . . ወዘተ መድብለ ጸጋ ያላት ናት፡፡ ቤተ ክርስቲያን ይህንን ሀብት በአግባቡ እንድትጠቀምበት መመርመር፤ ለቀጣዩ ትውልድ የእውቀት ምንጭ በሚሆን መልኩ ማደራጀትና ማስተባበር የሚጠበቅ ሥራ ነው፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ይህንን ፈርጀ ሰፊ ሀብት ለልማት ለማዋል ወቅታዊና ነባራዊ ችግሮችን በጥናትና ምርምር በታገዘ መልኩ ለመፍታት መንቀሳቀሱ ይበል የሚያሰኝ ነው፡፡” በማለት የገለጹ ሲሆን የጥናት መጽሔቱ ለኅትመት እንዲበቃ ከፍተኛ ሚና የተጫወቱትን አካላት አመስግነዋል፡፡

 

መጽሔቱ ብፁዕ አቡነ ሉቃስ የሰቲት ዑመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና በማኅበረ ቅዱሳን የጥናትና ምርምር ማእከል አማካሪ ቦርድ ሰብሳቢmetshate አማካይነት ተባርኮ የተመረቀ ሲሆን በሰጡት ቃለ ምእዳን “የማር፣ የአትክልት፣ የገብስ ጭማቂ መጠጣት የተለመደ ነው፡፡ ትልቁ ጭማቂ ግን ከሰው አእምሮ የፈለቀውን መጠጣት ነው፡፡ ያውም ከሊቃውንቱ የመነጨውን፡፡ ታሪካችን እንዲጠበቅ ያደርጋልና፡፡ ይህ የጥናት መጽሔት ብዙ ምርምር የተደረገበትና ለቤተ ክርስቲያን፣ ለአገር እድገት፣ በአጠቃላይ የቤተ ክርስቲያናችን ትውፊት፣ ባሕል፣ ወግና እምነት ተጠብቆ እንዲሸጋገር የሚያደርግ፤ ለትውልዱ ለማስተላለፍ የሚጠቅም ነው” ብለዋል፡፡

 

የጥናት መጽሔቱን ለማዘጋጀት በተደረገው ጥረት ከፍተኛ ትብብር ሲያደርጉ የነበሩ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ምሁራን እንዲሁም ተሳታፊዎች በጥናት መጽሔቱ ላይ አስተያየታቸውን የሰጡ ሲሆን፤ ከእነዚህም መካከል ሎሬት ፕሮፌሰር ጥሩሰው ተፈራ የጥናት መጽሔቱ ስለሚኖረው ጠቀሜታ ሲገልጹ “ጥናትና ምርምር ለአንድ ሀገር መሠረት ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን ብዙ የእውቀት ክምችቶች አሉ፡፡ ከምሁራን ብዙ ጠይበቃል፡፡ የጥናት መጽሔቱም ለቤተ ክርስቲያንም ሆነ ለሀገራችን ትልቅ አስተዋጽኦ የሚያደርግ ነው፡፡ በእኛ በኩል ድጋፍ ለመስጠት ዝግጁዎች ነን” በማለት ተናግረዋል፡፡

 

በጥናት መጽሔቱ ላይ በመሳተፍ ጊዜያቸውን፣ እውቀታቸውን በማካፈልና በማዘጋጀት ከፍተኛ ሚና ለነበራቸው ወንድሞችና እኅቶች እንዲሁም ድርጅቶች ከብፁዕ አቡነ ሉቃስ የሰቲት ዑመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና በማኅበረ ቅዱሳን የጥናትና ምርምር ማእከል የአማካሪ ቦርድ ሰብሳቢ፤ እንዲሁም ከብፁዕ አቡነ ኤልያስ የሰሜን ኦሞ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እጅ ማእከሉ ያዘጋጀላቸውን የምስክር ወረቀት ተቀብለዋል፡፡

 

በዚሁ ወቅት ብፁዕ አቡነ ኤልያስ የሰሜን ኦሞ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በሰጡት ቃለ ምእዳን “ይህች የጥናት መጽሔት ገና ካፊያ ናት፡፡  ኢትዮጵያ ያላት ሀብት እንደ ውቅያኖስ ተቀድቶ የሚያልቅ አይደለም፡፡ ኢትዮጵያ በቤተ ክርስቲያኒቱ ሳንባ ነው የምትተነፍሰው፡፡ መኩሪያዋም መመኪያዋም ቤተ ክርስቲያን ናት ገና ብዙ ይቀራል ይቀጥላል” ብለዋል፡፡

 

metshate 2በመርሐ ግብሩ ላይ የማኅበረ ቅዱሳን የመዝሙር ክፍል አባላት ያሬዳዊ ዝማሬ ያቀረቡ ሲሆን የጥናትና ምርምር ማእከሉ ዋና ዳይሬክተር ዮሐንስ አድገ በጥናቱ ላይ የተሳተፉትን፤ የማማከር ሥራ ያከናወኑትን፤ መጽሔቱን በመገምገም ሙያዊ ድጋፋቸውን በመስጠት ለተባበሩት ምሁራን ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

 

በመጨረሻም በብፁዕ አቡነ ሉቃስ የሰቲት ዑመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና በማኅበረ ቅዱሳን የጥናትና ምርምር ማእከል የአማካሪ ቦርድ ሰብሳቢ ቡራኬና ጸሎት የመርሐ ግብሩ ፍጻሜ ሆኗል፡፡

ማኅበሩ በሬድዮ ማሰራጫው ላይ የአየር ሞገድ ለውጥ አደረገ፡፡

ጥቅምት 8 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ

በማኅበረ ቅዱሳን ኅትመትና ኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ የሬድዮና ቴሌቪዥን ዝግጅት ክፍል ዘወትር አርብ ከምሽቱ 3፡30 እስከ 4፡30 ያሰራጭ የነበረውን ትምህርታዊ የሬድዮ ዝግጅት የአየር ሞገድ ለውጥ በማድረግ በ19 ሜትር ባንድ 15335 ኪሎ ኸርዝ አጭር ሞገድ አማካኝነት በተሻለ ጥራት ከጥቅምት 9/2005 ዓ.ም. ጀምሮ ማስደመጥ እንደሚጀምር በማኅበረ ቅዱሳን የሬድዮና ቴሌቭዥን ፕሮግራም አስተባባሪ ዲ/ን ሄኖክ ኀይሌ አስታወቁ፡፡ እንዲሁም ከዚህ ቀደም የተላለፉ መርሐ ግብሮችን www.dtradio.org ላይ መከታተል እንደሚቻል አያይዘው ገልጸዋል፡፡

ከሰባት ሺህ በላይ በሌላ እምነት የነበሩ ሰዎች ተጠመቁ

ጥቅምት 8 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ

 

በደቡብ ኦሞ ሀገረ ስብከት ባሳለፍነው የ2004 ዓ.ም. ቁጥራቸው ሰባት ሺህ አንድ መቶ አርባ አንድ ሰዎች የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ሃይማኖት በመቀበል መጠመቃቸውን የሀገረ ስብከቱ ሪፓርት አመለከተ፡፡

 

የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ትጉሀን ወንድወሰን ገ/ሥላሌ ለ31ኛው የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ መንፈሳዊ ጉባኤ ባቀረቡት ሪፓርት የሕግ ታሪሚዎች በተለያዩ ቤተ እምነቶች ውስጥ ከነበሩ ሰዎች መካከል ሰባት ሺህ አንድ መቶ አርባ አንድ ሰዎች ሊጠመቁ ችለዋል” ብለዋል፡፡

የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ የከሰዓት በኋላ ውሎ

ጥቅምት 6 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ


31ኛው የመንበረ ፓትርያርክ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ከዛሬው የከሰዓት በኋላ መርሐ ግብሩ ላይ የትግራይ ማእከላዊ ዞን፣ /የአክሱም/፣ የሲዳሞ፣ የሰሜን ጎንደር፣ የምሥራቅ ሐረርጌ፣ የጅማ ዞን፣ የመቀሌ ዞን፣ የኢሊባቡር፣ የድሬዳዋ፣ የጋሞ ጎፋ፣ የሰሜን ወሎ፣ የባሌ፣ የደቡብ ጎንደር የምሥራቅ ወለጋ፣ የአርሲ፣ የትግራይ ምሥራቅ ዞን /የአዲግራት/፣ አህጉረ ስብከቶች የበጀት ዓመቱን ሪፓርታቸውን በሥራ አስኪያጆቻቸው አማካኝነት ለጉባኤው አቅርበው መርሐ ግብሩ በጸሎት ተፈጽሟል፡፡ 31ኛው መደበኛ ጉባኤ ነገ ጧት 2፡30 ላይ ይቀጥላል፡፡

ቤተ ክርስቲያንን ጠብቋት

ጥቅምት 6 ቀን 2005 ዓ.ም.

አባ ዘሚካኤል

ቅድሚያ ለቤተ ክርስቲያን እንቁም! ምን እንደምትልም እንጠብቃት (እንስማት)!

“ወይእዜኒ ዕቀቡ ርእሰክሙ ዘሎቱ ሤመክሙ መንፈስ ቅዱስ ጳጳሳተ ከመ ትርአዩ ቤተ ክርስቲያኑ ለክርስቶስ እንተ አጥረያ በደሙ፤ በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ትጠብቋት ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመባት ለመንጋው ሁሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ” (የሐዋ.20፥28)፡፡

 

ፓትርያርክ ለመሾም:-

  • ሁሉም ድርሻው እስከምን እንደሆነ ይወቅ!
  • የሲመቱ ሂደት ምንም ይሁን ምን የተዋሕዶ ምእመናንን ሊከፋፍል በሚችል መንገድ ለሚሠሩ በር አንክፈት!
  • አንድነታችን የበለጠ እንዲጸና እንጸልይ!

 

ወይእዜኒ ዕቀቡ ርእሰክሙ፡ ’አሁንም ራሳችሁን ጠብቁ’ የግእዙ ትርጓሜ ሲል’፣ በአማርኛው መጽሐፍ ቅዱስ ’ለራሳችሁ ተጠንቀቁ’ ይላል፡፡

 

ቅዱስ ሉቃስ እንደጻፈው፣ የቅዱስ ጳውሎስን የማስጠንቀቂያ ምክር በጊዜው የመንጋው ጠባቂ ለሆኑት አባቶች መጀመሪያ “ራሳችሁን ጠብቁ’ ነው ያላቸው፡፡ በመሆኑም ይህን የቅዱስ ጳውሎስ ምክር የተረዱ አባቶቻችን ከሁሉ በፊት  ራሳቸውን በመልካም መንገድ ማቆምን ቅድሚያ ሰጥተዋል፡፡ በመሆኑም ራሳቸውን ከእምነት ለመለየት ከሚፈታተኗቸው:-በሥጋዊ ድካም ከሚመጡ ይሁን በሌሎች ውጫዊ ምክንያቶች ከሚነሡ እኩያት አሳቦችና ተግባራት ራሳቸውን ጠብቀው ይኖራሉ። ከሌላ ስለሚመጣው ፈተና ምክንያት ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ይላል ”ወአነ አአምር ከመ ይመጽኡ እምድህሬየ ተኩላት መሰጥ እለ ኢይምህክዋ ለመርዔት፤ ከኔ በኋላ ለምእመናን የማያዝኑ ሰውን እየነጣጠቁ ወደ ገሃነም የሚያወርዱ ሐሰተኞች መምህራን እንዲነሡ አውቃለሁ” (ማቴ፣ 7: 15) ይላል፡፡ ከዚህ የምንረዳው ዋናው ነገር ሐሰተኛ መምህራን ሊያሳስቱ የሚሞክሩት ምእመናንን ብቻ አይደለም ታላላቆችንም ነው እንጂ፤ ከዚህ በፊት ከታየው ልምድ ለቤተ ክርስቲያን የጠቀሙ በመምሰል አባቶችን ወደ አላሰቡት ስህተት የሚጥሉ አሉ፣ ሰይጣን እንኳን ሁሉን ቻይ የሆነውን አምላክ ሊፈታተን ቀርቦ የለምን? ከላይ በተመሳሳይ ”ከኔ በኋላ ለምእመናን የማያዝኑ ሰውን እየነጣጠቁ ወደ ገሃነም የሚያወርዱ ሐሰተኞች መምህራን እንዲነሡ አውቃለሁ” ተብሏልና፡፡  ስለዚህ ቤተ ክርስቲያንን የሚጎዳ ነገር ለምሳሌ፣ መከፋፈል እንዲፈጠር ሊያደርግ የሚችል ምክንያት እንዳይገኝ በየግል መጠንቀቅ ተገቢ ነው፡፡ ቀጥሎም ጳጳሳትን በቡድን ማለትም ሲኖዶሱን ’ራሳችሁን ጠብቁ’ ማለት በመካከል የሚፈጠር አለመግባባት እና ሌላም ምክንያት እንዳይለያያችሁ ቀድማችሁ ጥንቃቄ አድርጉ ሲል ነው፡፡ በመከፋፈል ለሰይጣንና ለሠራዊቱ የተከፈተ በር፣ ከተከፈተ በኋላ እንኳን መልሶ ለመዝጋት ይቅርና የበሩን መዝጊያውን ለማግኘት የሚቸግር ይሆናል፡፡ ካለፈው የመከፋፈል ልምድ እንደ ተረዳነው፣ በሁለት መከፈል ሳይበቃ መዘዙ ወደ ብዙ ትንሽ ክፍፍል ጭምር ማምራቱን  መዳኘትና መግታት ወደ ማይቻልበት ደረጃ ተደርሷል፡፡ ይህ ሁኔታ ወደፊት ምን ሊሆን እንደሚችል አምላክ ብቻ ነው የሚያውቀው፡፡ ስለዚህም እግዚአብሔርን ሁል ጊዜ በጸሎት እንጠይቀው፡፡

 

“ወኵሎ መራዕየ፣ ምእመናንን ሁሉ ጠብቁ፡፡ ዘሎቱ ሤመክሙ መንፈስ ቅዱስ ጳጳሳተ፣ መንፈስ ቅዱስ ጳጳሳት አድርጎ የሾማችሁ እናንት ዕቀቡ ጠብቁ” ብሎአል፡፡ የቤተ ክርስቲያን ሹመት ከመንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ ማንም ሰው ደግም ይሥራ ክፉ፣ የሚሾመው ከመንፈስ ቅዱስ ነው፡” ከመ ትርአዩ ቤተ ክርስቲያኑ ለክርስቶስ እንተ አጥረያ በደሙ፣ በወርቀ ደሙ የዋጃትን የምእመናንን አንድነት ትጠብቋት ዘንድ የሾማችሁ፡፡” አባቶች የሚጠብቁት የእግዚአብሔር መንጋ የሆኑትን ምእመናንን ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያንም ስንል የምእመናን አንድነት በመሆኑ፣ ከአባቶች ጠብቆት ውስጥ ምእመናንን ከመከፋፈል፣ ከኑፋቄ፣ ወዘተ በሽታ መከላከል ዋናው ተግባር ነው፡፡ ያለፉት ዘመናት ምእመናን በሀገር ውስጥ ሲኖዶስ፣ በውጭ እና ከዚህም ከዚያም የሌለ በሚል ተከፋፍለን በመለያየት ተውጠን ከርመናል፡፡ እግዚአብሔር ሲኖዶሱን” ወኵሎ መራዕየ፣ ምእመናን ሁሉ ጠብቁ” በማለቱ ሁሉም ምእመናን ከመሰናከል የሚድኑበት፣ ከፋፋዮች ምክንያት የሚያጡበት፣ መናፍቃን የሚያፍሩበት፣ አንድነትን የሚያመጣ ቁርጥ ውሳኔ የሚሻበት ወቅት ነውና መንጋው በመከፋፈል ከመጥፋት አባቶች እንዲታደጉት ጊዜው ግድ ይላል፡፡

 

የመንጋው ጠባቂዎች የተባሉት ቅዱስ ሲኖዶስ በዋናነት ሲሆን ከሊቃነ ጳጳሳት ቀጥሎ በቤተ ክህነት የመምሪያ ሓላፊዎች በተዋረድም ሀገረ ስብከት፣ ወረዳ ቤተ ክህነትና አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን የሚያገለግሉትን ሲሆን፣ እንዲሁም የእግዚአብሔር መንጋ የተባሉት መላው የኢትዮጵያ ኦርቶዶስ ተዋሕዶ ምእመናንን ሁሉ ያጠቃልላል፡፡ ከነዚህም ዋና ውሳኔ ሰጭው የሆነው ቅዱስ ሲኖዶስ ነው፡፡

 

ቅዱስ ሲኖዶስ የፓትርያርኩ፣ ሊቃነ ጳጳሳት፣ ኤጲስ ቆጶሳት መሪው መንፈስ ቅዱስ የሆነ ዐቢይ ጉባኤና የቤተ ክርስቲያኒቱ የመጨረሻ ከፍተኛ የሥልጣን ባለቤት ነው፡፡ በማንኛውም የቤተ ክርስቲያኒቱ ጉዳይ በቅዱስ ሲኖዶስ የሚወሰነው ውሳኔ የመጨረሻ ውሳኔ ይሆናል፡፡ ፓትርያርኩ ተጠሪነታቸው ለቅዱስ ሲኖዶስ በመሆኑ የቅዱስ ሲኖዶሱን ውሳኔ ሊለውጡ አይችሉም፡፡ፓትርያርኩንም መርጦ የሚሾመው ይኸው ጉባኤ ነውና፡፡ ሁሉም ክርስቲያን በእኩል መረዳት ያለበት የሲኖዶስ አባላት ሲመረጡ እንደ ሕግ እግዚአብሔር መሆኑንና እግዚአብሔር ሳይፈቅድ ጳጳስ መሆን እንደማይቻል ነው፡፡ ሁለተኛም የተሰጣቸው ሓላፊነት ከእግዚአብሔር እንደመሆኑና የዘወትርም ሥራቸው በመሆኑ፣ ሁልጊዜም መንጋውን በመጠበቅ ለቤተ ክርስቲያን ስጋት የሆነውን ጉዳዮች በመለየት ጥንቃቄ ያደርጋሉ ብለን ማመን ይኖርብናል፡፡

 

እኛ ምእመናንም ደግሞ ማሰብ ያለብን አይነተኛ ነገር አለ፣ ይህም ለመንጋው ጠባቂዎች በትክክል ታዛዣቸው ነን? በጎቻቸው ነን ወይ?  ብለን እራሳችንን መመርመር አለብን፡፡ ለንባብ የበቃ የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ እንኳን እንደሚታየው ትኩረት ሳይሰጠው ከመታለፉ አልፎ እንደውም ማጣጣል ሲደረግበት ነው የሚስተዋለው፡፡ በመሆኑም አንዳንድ ጊዜ አባቶቻችንን እንድንጠራጠር የሚያደርጉንን ወሬዎችን በመስማት ወሳኞቹ እኛ ሳንሆን አስቀድመን መሆን አለበት ብለን ወስነን ቅዱስ ሲኖዶስ ከሚወስነው ጋር እንዳንጋጭ ከወዲሁ፣

 

  1. ከማን መስማት እንዲገባን መመርመር የለብንም ይሆን?

  2. አስቀድመን ለመወሰንስ እኛ ማን ነን?

  3. የቅዱስ ሲኖዶስ ከሳሽ መሆን ይጠቅመን ይሆን?

  4. የቅዱስ ሲኖዶስ መሪ መንፈስ ቅዱስ ነው ካልን መንፈስ ቅዱስ አይጠብቃቸውምን?

  5. ቤተ ክርስቲያን የሾመቻቸው ሊቃውንት ከሃምሳ በላይ ሊቃነ ጳጳሳት አንድ ላይ ሆነው መክረው የሚወስኑት ውሳኔ ሳንቀበል በአንድ ሚዲያ ላይ አሰማምሮ ወይም አጣጥሎ በተጻፈ ጽሑፍ የምንረበሽ እና የምንፈተን ከሆን ስህተቱ የማን ይሆን?

  6. መረጃዎችን ማወቅ ጥሩ ሲሆን፣ ነገር ግን ከእምነት አንጻር የቅዱስ ሲኖዶስን ውሳኔ የማጣጣል ሁኔታ የመልካም ይሆን?

 

የመሳሰሉትን ጥያቄዎች ማንሣትና ቀድሞ ሰው ካለው ልምድ እንዲሁም ከሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን አንጻር መጪውን ጊዜ ለቤተ ክርስቲያን ጥቅም ከቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ጋር መቆም እንዴት ይኖርብን ይሆን? ብለን ማሰብ ይኖርብናል፡፡ ምክንያቱም እስከ አሁን ከተለያዩ ጽሑፎች እንዳነበብነው፣ ከተለያዩ አስተያቶች እንደ ሰማነው፣ በጣም የሚገርመው መቼም፣ ምንም ሊጣጣሙ የማይችሉ አሳቦች ከተለያዩ ጽንፈኞች ሲቀርቡ ተስተውለዋል፡፡ ለምሳሌ፣ ባንድ ወገን መጀመሪያ እርቁ ይቅደም በሚል በሚገባ መረጃ አሳማኝ ነገር ሲቀርብልን በሌላ ወገን የእርቁ አካላት የተባሉ ጨርሶ የእርቅ አሳብ እንዳልተነሣ ሁሉ እንደገና ለእርቁ መፈጸም እንቅፋት ይሆናል ተብሎ የሚገመት ሁኔታ አደረጉ ወይም ለአዲስ መለያየት መንገድ ይከፍታል የሚያሰኝ መረጃ ተቀናብሮ የቀረበ ስናይ እንዴት ይሆን ይህ አሳብ የሚታረቀው? መቼ ይሆን እርቁ የሚፈጸመው? የሚል ጥያቄ እንድናነሣ ሁላችንንም ግድ አይለን ይሆን? በዚህ የተዘበራረቀ ሁኔታ አባቶችስ የምርጫውን ጉዳዩ እስከ መቼ ሊያቆዩት ይችሉ ይሆን? በዚህ ሁኔታ ላይ ባለድርሻ አካላት ሳያምኑበትና በወቅቱ ለቤተ ክርስቲያን ይጠቅማታል ብለው ባልወሰኑት የኛ ማጉረምረም ምን ጽድቅ ይፈጽም ይሆን? ሁል ጊዜም ቤተ ክርስቲያንን የሚጎዳት አባላቶቿ ከአባቶች መንፈሳዊ እልባትና ከቅዱሳት መንፈሳውያን መጻሕፍት ምክር ይልቅ በዓለማውያን ፍልስፍና ስንደገፍ መሆኑን አንዘንጋ፡፡ ነገር ግን መጽሐፍ ”እኛ ግን ከእግዚአብሔር እንዲያው የተሰጠንን እናውቅ ዘንድ ከእግዚአብሔር የሆነውን መንፈስ እንጂ የዓለምን መንፈስ አልተቀበልንም። መንፈሳዊውን ነገር ከመንፈሳዊው ነገር ጋር አስተያይተን መንፈስ በሚያስተምረን ቃል ይህን ደግሞ እንናገራለን እንጂ የሰው ጥበብ በሚያስተምረን ቃል አይደለም። ለፍጥረታዊ ሰው የእግዚአብሔር መንፈስ ነገር ሞኝነት ነውና አይቀበለውም፤ በመንፈስም የሚመረመር ስለ ሆነ ሊያውቀው አይችልም። መንፈሳዊ ሰው ግን ሁሉን ይመረምራል ራሱ ግን በማንም አይመረመርም። እንዲያስተምረው የጌታን ልብ ማን አውቆት ነው? እኛ ግን የክርስቶስ ልብ አለን” (1 ቆሮ 2: 13-16) ይለናል።

 

ሌላው ትኩረት የሚያሻው ጉዳይ የተለያዩ ግለሰቦችና ድርጅቶች ይጠቅማል ያሉትን ከምርጫው ጋር የተያያዙ የተለያዩ አሳቦች ሲያቀርቡ ተስተውለዋል፡፡ ግብአቱ መልካም ነው፣ በተለይ ሚዲያዎችን የሚከታተሉ ምእመናን፣ የሚጻፉ አሳቦችን ሁሉ ከቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ በላይ በማድረግ የማየቱን ጉዳይ ነው፡፡ መረዳት ያለብን ፍሬ አሳብ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት በሚዲያ እንደተጻፈ ሊያውቁም ላያውቁም ይችላሉ፣ በግድም የማወቅ ግዴታ የለባቸውም፡፡ ብፁዓን አበው የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ሥራቸውን መሥራት አለባቸው እንጂ ተቀባይነትን ለማግኘት ሁል ጊዜ ወደ ሚዲያ መቅረብ አለባቸው አንልም፡፡ በየሚዲያዎች ሁሉም እንደፈቃዱ የጻፈውን ሁሉ ለማስፈጸም ደፋ ቀና ማለት አለባቸውም ልንል አይገባም፡፡ ከማንም ይልቅ በቤተ ክርስቲያን ሕግና ጊዜውን በዋጀ ውሳኔ ቤተ ክርስቲያንን መምራት ስላለባቸው ረድኤተ እግዚአብሔርን አጋዥ በማድረግ ውሳኔዎችን ያሳልፋሉ፡፡ በአባቶች ውሳኔ ማንም ጣልቃ መግባት የለበትም፡፡ የሚወሰነውን ሁሉ በእውነት ክርስቲያን የሆነ ሁሉ በአግባቡ መቀበል ይኖርብናል፡፡ ሁሉም እንዲህ ቢያረግ ማለትም ለቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ቢገዛ ቤተ ክርስቲያን አንድነትዋ ይጠበቃል፣ መለያየት አይኖርም፣ አንድነታችን ይጸናል፣ ከፋፋይ ያፍራል፣ ይልቁንም ሰይጣን ይመታል፣ በመስቀሉ እውነተኛ ፍቅር ይቀጠቀጣል፡፡ እግዚአብሔር አምላክ የሚለየንን ሰይጣን ይቀጥቅጥልን!!!

 

በመሆኑም ቅዱስ ሉቃስ” ያመኑትም ሕዝብ አንድ ልብ አንዲትም ነፍስ ነበሯቸው (የሐዋ. ሥራ.4፥32)” እንዲል፤ በአንድ ሲኖዶስ ውሳኔ ማዘዝና መታዘዝ ስንተዳደር ነው ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን የሚከበረው፡፡ ይህ ሲሆን ነው ፍቅርና አንድነት የሚመጣው እንጂ በየቦታው ለራሳችን እንደ ራሳችን አሳብ መምህር ካቆምን እንናገራለን እንጂ በሕይወታችን ዘመን እርቅና አንድነትን ሳናያት ልናልፍ እንችላለን፡፡ እግዚአብሔር በሕይወታችን ዘመን የቤተ ክርስቲያንን አንድነቷን ያሳየን!!! ሳናይ አይውሰደን ብለን መመኘትና መጸለይ ይገባናል፡፡

 

ባጠቃላይም የአሁኑ ወቅታዊው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጉዳይ፣ የፓትርያርክ ምርጫ ጉዳይ ነው፡፡ ሁሉም እንደሚለው፣ በዓለም ያሉ የቤተ ክርስቲያኗ ልጆች ሁሉ በጉዳዩ ያገባቸዋል፤ (ይህንን ስንል ተመሳስለው የቤተ ክርስቲያኗ ልጆች በመምሰል የኑፋቄና የጸብ መንገድ ሁል ጊዜ የሚምሱትን ሳይጨምር መሆኑን መገንዘብ ያሻል)፡፡  ነገር ግን በፓትርያርክ ምርጫ እያንዳንዱ ሰው ድርሻው እስከምንድነው? የዚህ ጥያቄ ምክንያት፣ ምእመናን በተለይ በውጭ አገር ያሉ የተለያየ ሚድያ ስለሚከታተሉ፤ ሚዲያዎቹ በአንድ በኩል የቤተ ክርስቲያኗን ጥቅም የሚፈልጉ ሲሆኑ፣ ሌሎቹ  የፖለቲካ፣ የተሐድሶ ወዘተ ዓላማና ጥቅም ያላቸው ከወዲሁ ምርጫው ከመካሄዱ በፊት የራሳቸውን ግምት በመስጠት ምእመናንን የሚያንጽ ወይም የሚረብሽ አሳብ ስለሚበትኑ፤ ከዚህ የተነሣ አንዳንድ ግለሰቦች በራሳቸው ፓትርያርክ የመረጡ ያህል እከሌ ይሁን እስከ ማለት የደረሱ አሉ፡፡ በመሆኑም ከቤተ ክርስቲያን ሥርዓት አንጻር የፓትርያርክ ምርጫ ሥርዓትን በመረዳት:-

 

  • ሁሉም ድርሻው እስከምን እንደሆነ ይወቅ!
  • የሲመቱ ሂደት ምንም ይሁን ምን የተዋሕዶ ምእመናንን ሊከፋፍል በሚችል መንገድ ለሚሠሩ በር አንክፈት!
  • አንድነታችን የበለጠ እንዲጸና እንጸልይ!
  • በተለያየ ቤተ ክርስቲያንን በማይወክሉ ሚዲያዎች የሚቀርቡ ነገሮች ሁሉ እንደ ቤተ ክርስቲያን ውሳኔ ሊታዩ አይችሉምና በጥንቃቄ መረጃዎችን እንይ
  • ምእመናንን ሊከፋፍል የሚችሉ ወሬዎች እየተለቀቁ ስለሆነ በጥንቃቄ እንከታተል
  • ሚዲያዎችም ጥንቃቄ ቢያደርጉ በጎ ሚያሰኝ ነው፣ ምእመናንን በመከፋፈል የሚገኝ ጽድቅ የለምና፡፡
  • እግዚአብሔር ከፈቀደው በቀር ማንም ሊመረጥ አይችልምና ከወዲሁ ተረብሸን የወደፊቱ ክርስትናችን ፍቅር የጎደለው እንዳይሆን እንጠንቀቅ
  • ሊመርጡ /ሊወስኑ/ ለሚችሉ ባላደራዎች ፈንታውን እንስጥ እንጂ በማንወስነው ጉዳይ አስቀድመን አንፈርጅ
  • ይልቁንም ሁሉን ማድረግ ለሚቻለው እግዚአብሔር አደራ እንስጥ፡፡

 

በዚህ በቃ ይበለን! ከዚህ በላይ በመከፋፈልና በመለያት እግዚአብሔር የቤተ ክርስቲያንን ጥፋት አያሳየን!!!

 

ወስብሐት ለእግዚአበሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመሰቀሉ ክቡር አሜን!!!

የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ መንፈሳዊ ጉባኤ 31ኛ መደበኛ ስብሰባ ዛሬ ጥቅምት 6 ቀን 2005 ዓ.ም. ጧት 3 ሰዓት ላይ በተካሄደው ጸሎት ተከፈተ፡፡

ጥቅምት 6 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ


ጉባኤው ከዛሬ ጥቅምት 6 ቀን ጀምሮ እስከ ቅዳሜ ጥቅምት 11 ቀን ድረስ በጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ ይካሄዳል፡፡ በጠቅላይ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ አማካኝነት አምስት አባላት ያሉበት አርቃቂ ኮሚቴ የተሰየመ ሲሆን፤ ይህንኑ ተከትሎ ብፁዕ አቡነ ናትናኤል ዐቃቢ መንበረ ፓትርያርክ የጉባኤው መክፈቻ ቃለ ቡራኬ ሰጥተዋል፡፡ ብፁዕ አቡነ ናትናኤል በዚሁ ቃለ ቡራኬያቸው “በዚህ ጉባኤ የታደማችሁ አባቶቼ ወንድሞቼ እንኳን ለዚህ ቀን አደረሳችሁ፡፡” ካሉ በኋላ  “ሐዋርያዊት የሆነች የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በቀኖናዋ ቅዱሳን ያሰኘቻቸው ልጆቿ አያሌ ናቸው፡፡ ቅድስናናን የሚያሰጠው የቤተ ክርስቲያናችን ትውፊት ጠብቀን በቤተ ክርስቲያናችን ሊሠራ የሚገባውን ወስነን እንሠራለን” ብለዋል፡፡

 

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በ2005 ዓ.ም. ለመፈጸም ያሰበቻቸውን የዕቅድ ሪፓርት በብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጅ አቡነ ፊሊጶስ የቀረበ ሲሆን ብፁዕነታቸው “በልዑል እግዚአብሔር አባታዊ ፈቃድ ከሐምሌ ወር 2003 እስከ ሰኔ 30 ቀን 2004 ዓ.ም. ወጥተን ወርደን ለቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን እድገትና ልማት፣ በሕዝባችን ሰላምና አንድነት፣ ሠርተን የሥራችንን የሥራ ክንውኖችና ውጤቶች እንደ አንድ ልብ መካሪ፣ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ሆነን ለመገምገም ያበቃንንና የሰበሰበንን አምላክ ደግመን ደጋግመን እናመሰግናለን” ብለዋል፡፡ በብፁዕ ሥራ አስኪያጅ ጋባዥነትም በአቶ ተስፋዬ ውብሸት የጠቅላይ ቤተ ክህነት ምክትል ሥራ አስኪያጅ የ2004 ዓ.ም. በጀት ዓመት የሥራ ክንውን አጠቃላይ ሪፓርት ቀርቧል፡፡ ምክትል ሥራ አስኪያጁ በሪፓርታቸው፡- “ቅርሶችን በዓለም ዐቀፍ ምዝገባ ሰነድ ለማስያዝና የደመራ መስቀል በዓላችንን በዮኔስኮ ለማስመዝገብ ዝግጅቱ ተጠናቋል፡፡ እንዲሁም የቅዱስ ያሬድ ዜማንና ሥርዐቱን ፊደላትና አኀዞችን የጥምቀት በዓልንም በቀጣይ ለማስመዝገብ ጥናቱ ተፈጽሟል” ብለዋል፡፡ አቶ ተስፋዬ በልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን አማካኝነት በ2004 ዓ.ም. የተሠራውን አስመልክቶ ሲናገሩ “በተቀናጀ የገጠር ልማት 26,864,687.00/ በመመደብ 923,254 ሰዎችን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ዐሥር ፕሮጀክቶችን በተለያዩ ክልሎች ዘርግቶ ሠርቷል፡፡ ኮሚሽኑ በበጀት ዓመቱ፣ በተቀናጀ የገጠር ልማት፣ በውኃ አቅርቦትና ንጽሕና አጠባበቅ፣ ኤች አይ ቪ ኤድስን በመከላከል፣ በገዳማት ልማት፣ በስደተኞችና ከስደት ተመላሾች ክብካቤና ድጋፍ 26 ፕሮጀክቶን ዘርግቶ በ120,955,270.00 ብር በጀት ተግባራዊ አድርጓል” ብለዋል፡፡ ከሻይ እረፍት መልስ “ግጭት፣ የግጭት መንስኤና አፈታት” በሚል ርዕስ በልማት ኮሚሽን የስደተኞች ጉዳይ ሓላፊ አቶ ይልቃል ሽፈራው አማካኝነት ቀርቦ በብፁዕ አቡነ ሳሙኤል አማካኝነት ጉባኤው ተወያይቷል፡፡

 

ከምሳ ሰዓት በፊት የነበረው መርሐ ግብርም 6 ሰዓት ከሃያ ላይ በጸሎት ተዘግቷል፡፡

የመጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር ዓመታዊ ጉባኤውን አካሄደ

ጥቅምት 6 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ

 

የኢትዮጵያ መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር ዓመታዊ ጉባኤውን ቅዳሜ ጥቅምት 3 ቀን 2005 ዓ.ም አዲስ አበባ በሚገኘው ሀርመኒ ሆቴል አካሂዷል፡፡ በጉባኤው ላይ ብፁዕ አቡነ ገብርኤል የቅዱስ ሲኖዶስ አባልና የሲዳማ ጌዲኦ ቡርጂና አማሮ ልዩ ልዩ ወረዳዎች  ሊቀ ጳጳስ እንዲሁም ዶክተር አባ ኀይለ ማርያም መልሴ የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ዲን ጨምሮ ከአብያተ ክርስቲያናት የተወከሉና የማኅበሩ አባላት ተገኝተዋል፡፡

 

የኢትዮጵያ መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር በአሁኑ ጊዜ በትርጉም፣ በኅትመትና በስርጭት ሥራ ላይ ከፍተኛ ትኩረት በመስጠት መጠነ ሰፊ እንቅስቃሴ እያደረገ እንደሚገኝ ያስታወሱት የማኅበሩ ዋና ጸሐፊ አቶ ይልማ ጌታሁን “በዘመናችን እየጨመረ የመጣውን የቅዱሳት መጽሐፍት ፍላጎት ስንመለከት ጥረታችንን ከጊዜ ወደ ጊዜ ማጠናከር እንዳለብን ይታመናል፡፡ ይህንን ተግባር ደግሞ በተገቢው መንገድ ለማከናወን ሁሉም ባለድርሻ አካላት ሓላፊነታቸውን ባግባቡ መወጣት ይኖርባቸዋል” ብለዋል፡፡ ማኅበሩ በያዝነው ዓመት በሰባት ዋና ዋና ዘርፎች ሊሠራቸው ያሰባቸውን ዕቅዶች በሪፖርታቸው ያካተቱት  ዋና ጸሐፊው፥ በአባላት ምዝገባና በቅስቀሳ ዘርፍ ሁሉንም ክርስቲያን ለማሳተፍ መጠነ ሰፊ ቅስቀሳና ምዝገባ ለማከናወን እንዳቀደ አስታውቀዋል፡፡

 

በኢትዮጵያ የመጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር፡- የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ጨምሮ የወንጌላውያን ኅብረትና የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን በአባልነት ተካተዋል፡፡

Dn. mulugeta

በአባቶች መካከል የተጀመረው የዕርቀ ሰላሙ ውይይት ተጠናክሮ እንዲቀጥል ተጠየቀ

ጥቅምት 2 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ


Dn. mulugetaየማኅበረ ቅዱሳን ሥራ አመራርና የሥራ አስፈጻሚ ጉባኤያት መስከረም 30 ቀን 2005 ዓ.ም. በጋራ ባካሄዱት ስብሰባ በአስተዳደርና በተወሰኑ የቀኖና ቤተ ክርስቲያን አተረጓጎም ልዩነት ምክንያት ለሁለት አሠርት ዓመታት ተለያይተው በቆዩ አባቶች መካከል የተጀመረው የዕርቀ ሰላም ውይይት እስከ መጨረሻው ተጠናክሮ እንዲቀጥል ጥያቄ አቅርበዋል፡፡ “የስብሰባው ዋነኛ አጀንዳ በአገር ውስጥና በውጪ አገር በሚገኙ አባቶች መካከል የተጀመረው ውይይት ከሁሉም ጉዳዮች በፊት ቅድሚያ ተሰጥቶት እንዲሠራና እንዲፈጸም የማኅበሩ ፍላጎት መሆኑን ለማስታወቅና እንደ ጥያቄም ለማቅረብ ነው፡፡” በማለት መስከረም 30 ቀን 2005 ዓ.ም. ስለተካሄደው ስብሰባ መግለጫ የሰጡት የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጸሐፊ ዲ/ን ሙሉጌታ ኀይለ ማርያም ናቸው፡፡

 

ዋና ጸሐፊው ለመካነ ድራችን በሰጡት መግለጫ “የማኅበሩ አባላትም ሆኑ ሌሎቹም ምእመናን የተጀመረው የዕርቀ ሰላም ውይይት በጥሩ ሁኔታ እንዲጠናቀቅ ተግተው መጸለይ ይገባቸዋል፡፡ በተጨማሪም የሰላሙንና የዕርቁን ሁኔታ ሊያደናቅፉ የሚችሉ ጉዳዮችን ከማድረግ መቆጠብ ይኖርባቸዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቱም አንድነቷ ተመልሶ የምትሠራበት ሁኔታ ይፈጠር ዘንድ ማኅበሩ የሚጠበቅበትን አገልግሎት ለመፈጸም ዝግጁ ነው፡፡ ስለሆነም የማኅበሩ አባላትና ደጋፊዎች እንዲሁም መምህራን ጭምር የማኅበሩን አቋም የማስታወቅ ሓላፊነት አለባቸው፡፡” ብለዋል፡፡

 

እርቁ እንዴት ይሁን? እንዴት ይፈጸም የሚሉ ጥያቄዎች ምላሽ የሚሰጣቸው በሁለቱም ቦታዎች በሚገኙ አባቶችና በአስታሪቂ ሽማግሌዎች መሆኑን በመገንዘብ ጉዳዩን ለሚመለከታቸው አካላት መተው እንደሚገባ ያስታወቁት ዲ/ን ሙሉጌታ የተጀመረው እርቅ እንዲጠናቀቅ ሁሉም ድጋፍ እንዲያደርግና እግዚአብሔርንም በጸሎት እንዲማጸን አሳስበዋል፡፡

 

ዋና ጸሐፊው በማጠቃለያ መልእክታቸው፡- “ፍቅር ሰላምና አንድነት ለቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን አገልግሎት ስምረት እጅግ በጣም አስፈላጊ ነገሮች ናቸው፡፡ ሁል ጊዜ ለፍቅር ለመግባባትና አብሮ ለመሥራት በሰላም ለመኖር ሁሉም መጣር ይኖርበታል፡፡ ስለዚህ ከዚህ የሚያደናቅፍ ሁሉ ከእግዚአብሔር አይደለም፡፡ አንድነትን የሚጠላ ፍቅርን የሚጠላ ሁሉ ከእግዚአብሔር አይደለም፡፡ ስለዚህ ሁሉም የቤተ ክርስቲያኒቱ ልጆች ለዚህ ጉዳይ መትጋት ይኖርባቸዋል” ብለዋል፡፡

እነሆ ክረምት አለፈ

 

ጥቅምት 1 ቀን 2005 ዓ.ም.

በመ/ር ምሥጢረ ሥላሴ ማናየ


“እነሆ ክረምት አለፈ ዝናሙም አልፎ ሄደ አበባው በምድር ላይ ታየ የመከር ጊዜ ደረሰ የቁርዬውም ድምጽ ተሰማ በለሱ ጎመራ ወይኖቹም አበቡ” መኀ.2፥11-13

 

ከዚህ ቀድሞ እንደተመለከትነው ክረምት ወርኀ ማይ/ውኃ/ ወርኀ ልምላሜ ወንዞች የሚሞሉበት ደመናና ጉም የሚሳብበት ሰማይ በደመና ተሸፍኖ የእግዚአብሔርን ጥበብ የሚያስተምርበት በመብረቅ በነጎድጓድ ድምጽ ታጅቦ ኀይለ እግዚአብሔርን የሚያስረዳበት መሆኑን ተመልክተን ነበር፡፡ አሁን ግን መግቦቱን ጨርሶ እነሆ ክረምት አለፈ ጊዜውንም በክረምት ከሚታየው ልምላሜ ቀጥሎ ለሚመጡ ለአበባና ለፍሬ አስረክቦ ከልምላሜ ቀጥለው የምናያቸው አበባና ፍሬ የሚያስተምሩት ቁም ነገር አለና፡፡

 

ከአበቦች ምን እንማራለን?

አበቦች ውብና ማራኪ አስደሳች ከመሆናቸው የተነሣ የሰው ልጅ በሙሉ አበቦችን ይፈልጋል ምድርም በአበቦች አጊጣ ተሸልማ ስትታይ ክረምት ከለበሰችው ልምላሜ ይበልጥ ታስደስታለች፡፡ “አሰርገዎ ለሰማይ በከዋክብት ወለምድርኒ አሰርገዋ በሥነ ጽጌያት” ሰማይን በከዋክብት አስጌጠው ምድርንም በአበቦች ደምግባት ሸለማት” ብሎ ቅዱስ ያሬድ ዘምሯል፡፡ ከዚህ የምንረዳው አምላካችን የሁሉ ጌጥ መሆኑን ነው፡፡ መጽሐፈ ኪዳን “ሠርጎ ዓለም ሣራሪሃ ለምድር ወኩሎ ተከለ ለሠርጎ ዓለም፡፡” የዓለም ጌጥ ምድርን የፈጠራት ሁሉንም ለዓለም ጌጥ ፈጠረ” ተብሎ ተጽፏል፡፡ በሜትር የማይለካ ሰማይን በከዋክብት፣ በፀሐይ፣ በጨረቃ ስፋቷ በዐይነ ገመድ የማይመጠን ምድር በአበባ ማስጌጥ ከቻለ ለሦስት ክንድ ከስንዝር የሆነ የሰውን ልጅ ማልበስ ማስጌጥ መሸለም ለምን አይችልም? ይችላል እንጂ፡፡ ታዲያ ከላይ የተመለከትናቸው ሁሉ የሚናገሩት የእግዚአብሔርን ከሓሊነት ነው፡፡ አፍ ሳይኖራቸው ይናገራሉ፤ አንደበትም ሳይኖራቸው ይመሰክራሉ፡፡

 

ከዚህ የተነሣ ጌታችን ሲያስተምር እንዲህ አለ “ወበእንተ አራዝኒ ምንተኑ ትሄልዩ ርዕዩ ጽጌያተ ገዳም ዘከመ ይልህቁ ኢይፈትሉ ወኢይጸምው ወባህቱ እብለክሙ ከመ ሰሎሞን ጥቀ ኢለብሰ በኩሉ ክብሩ ከመ አሐዱ እምዕሉ” ማቴ.6፥28፡፡

 

ስለ ልብስስ ለምን ትጨነቃላችሁ? የሜዳ አበቦችን ተመልከቱ! እንዴት እንደሚያድጉ ልብ አድርጋችሁ ተመልከቱ! አይደክሙም አይፈትሉም ነገር ግን እላችኋለሁ ሰሎሞን ስንኳን በክብሩ ሁሉ ከነዚህ እንደ አንዱ አልለበሰም” ብሎ አበቦች ከእግዚአብሔር አግኝተው ነው ጌጥን ውበትን ተጎናጽፈው የሚኖሩት ለእነዚህ አበቦች ውበትን መውደድን የሰጠ እግዚአብሔር ለእኛም ይሰጠናል ብሎ ማመን የሚገባ መሆኑን በመግለጽ ሰው ምን እለብሳለሁ በምን አጌጣለሁ ብሎ ከመጨነቅ ይልቅ እግዚአብሔር በተፈጥሮ ውብ አድርጎ የፈጠረው እንደሆነ በማሰብ የጎደለው ሁሉ ከእግዚአብሔር የሚገኝ እንጂ በጭንቀት በመወጠርና በማማረር እንደማይገኝ ይልቁንም አበቦችን እንዲህ ያስጌጠ አምላክ ለእያንዳንዳችን የሚያስፈልገንን ሁሉ መስጠት የሚችል መሆኑን ማወቅ የተሻለ ነው፡፡ የእኛ ድርሻ መቀበል እንጂ መጨነቅ ሊሆን እንደማይገባም ያስተምረናል አበቦች ይህን ውበት ያገኙት በመጨነቅ አይደለም ሰውስ ከአበባ እንዴት ያንሳል?

 

በትክክል ሰው አበባን ይመስላል አበባ ያብባል በመልካም መዓዛው ከሰው ጀምሮ እስከ ጥቃቅን ፍጥረታት ድረስ ይማርካል ከአበባ ላይ መስፈር የሚፈልጉት ንቦች ብቻ አይደሉም ትንኞችና ዝንቦችም ጭምር እንጂ፡፡ ንቦች ማር ይሠሩበታል ዝንቦችና ትንኞች ደግሞ ቆሻሻቸውን ያራግፉበታል፡፡ ከዚህ በኋላ አበባው ይጠወልጋል ይረግፋል የሚከቡት ንቦችም ሆኑ ትንኞችና ዝንቦች አይፈልጉትም፡፡ አበባ በጊዜ ማራኪና አስደሳች ቢሆን ሲደርቅ ግን የሚፈልገው የለም የሚረግጠው እንጂ፡፡ አበባ ሲደርቅ አበባ መሆኑ እንኳን ይዘነጋል፡፡ በዚያን ጊዜ ወዳጁ ሁሉ ይርቀዋል ያን ጊዜ ወዳጅ የሚሆነው መደፋት አሊያም እሳት ብቻ ነው፡፡

 

ሰውም በእውነቱ ይህን ይመስላል ሲወለድ እናት አባት ዘመድ አዝማድ ወዳጅ በመወለዱ ይደሰታል፡፡ ሲያድግ አንተ ልጅ የማነህ አቡሽዬ የሚለው የሚስመው የሚከበው ይበዛል ሁሉም ምነው እንደዚህ ልጅ በሆንኩኝ አይ ልጅነት እያለ ይመኛል፡፡ ልጁ ካደገ በኋላ ግን እንደ አበባው ደረቅ እያለ የሚያስከፋ የሚያሳዝን፣ የሚያሰቃይም ሕይወቱ አላዋቂ አጫጅ እንደ አጨደው የፈረስ ሳር  ምስቅልቅል ያለ ሀዘንና መከራ የከበቡት ይሆናል፡፡ ሆኖም ግን አበባውን ዝንቦች ትንኞች እንዲሁም ማር መሥራት የሚችሉ ንቦች እንደሚከቡት ሰውንም እንደመአር የሚጣፍጥ መልካም ሥራ እንዲሠራ የሚረዱት መላእክት ይከቡታል ይረዱታል፤ ይላላኩታል በአንጻሩ ደግሞ እንደ ቆሻሻ የኀጢአትን ክምር የሚጭኑበት አጋንንት እንደ ትንኝና ዝንብ ከበው ኅሊናውን በክፉ ሐሳብ ያቆሽሹታል፡፡ በመላእክት ተከቦና ታጅቦ መልካም ሥራ ሲሠራ እግዚአብሔርንም ሰውንም ራሱንም መላእክትንም ያስደስታል፡፡ በፍቅሩም አሕዛብን ይማርካል፡፡ በሌላ መልኩ አጋንንት እንደዝንቦችና ትንኞች በላዩ ላይ ሰፍረው የኀጢአት ቆሻሻቸው መጣያ አድርገውት ክፉ እየሠራ ሲታይ እግዚአብሔርንም መላእክትንም ሰውንም ያሳዝናል አበባው ደርቆ ሲወድቅ እንደሚያስጠላ እርሱም ያንን ይመስላል፡፡

 

ከዚህ የተነሣ ነው ኢሳይያስ እንዲህ ብሎ ያስተማረው “ሥጋ ለባሽ ሁሉ ሣር ነው ክብሩም ሁሉ እንደ ምድረ በዳ አበባ ነው፡፡ የእግዚአብሔር እስትንፋስ ይነፍስበታልና ሣሩ ይደርቃል አበባውም ይረግፋል በእውነት ሕዝቡ ሣር ነው፡፡ ሣሩ ይደርቃል አበባውም ይረግፋል” ኢሳ.40፥6-8 የሰው ልጅ ሕይወቱ እንዲህ እንደ ሣር ጠፊ እንደ አበባም ረጋፊ ከሆነ በዚህ ጊዜው ንስሐ መግባት ሥጋውን በልቶ ደሙን መጠጣት፤ ስርቆትን፣ ዝሙትን፣ ሐሰትን፣ ትዕቢትን፣ ተንኮልን፣ ክፋትን፣ ቂምን፣ በቀልን፣ ሥጋዊና ሰይጣናዊ ቅናትን አስወግዶ ወደ ፈጣሪው መቅረብ ይገባዋል፡፡ አበባ ዕድሜው አጭር ነው፡፡ ሰውም እንደዚያው ስለሆነ ሰው ሞትን መቅደም አለበት እንጂ ንስሐ ሳይገባ በሞት መቀደም የለበትም፡፡ ሰው በዕለት ከዕለት እንቅስቃሴው ሞትን ማሰብ መቻል ይገባዋል፡፡ “አብድ ውእቱ ዘይሄሊ ካልአ ዘእንበለ መቃብሩ ወርስቱ” እርስቱ ከሆነው ከሞትና ከመቃብር ሌላ የሚያስብ ሰነፍ ነው” እንዲል፡፡ ዮሐንስ አፈወርቅ

 

በሌላ መልኩ አበባን ስንመለከተው የሚወድቀው፣ የሚረግፈው ፍሬ ለማስገኘት ነው፡፡ አበባ ሲኖር በመአዛው ሰውን ያስደስታል፡፡ ሲረግፍም በፍሬው ይጠቅማል፡፡ ሰው ሲኖርም ሲሞትም ፈጣሪውን የሚያስደስት መሆን አለበት እንጂ ያለፍሬ ንስሐ መሞት የለበትም፡፡ “ግብሩኬ እንከ ፍሬ ሰናየ ዘይደልወክሙ ለንስሐ” ለንስሓ የሚገባ ፍሬ አድርጉ” ማቴ.3፥8

 

“እንግዲህ መልካም ፍሬ የማያደርግ ዛፍ ይቆረጣል፡፡ ወደ እሳትም ይጣላል ማቴ.3፥10 ተብሏልና፡፡ ሰውም መልካም ፍሬን አፍርቶ፣ ንስሐ ገብቶ፣ ተዘጋጅቶ፣ የሰማይ ቤቱን ሠርቶ፣ መንግሥተ ሰማያትን ሽቶ፣ ራሱን በንስሐ የተወደደ መሥዋዕት አድርጎ፣ ሰውቶ፣ ከእግዚአብሔር ተጠግቶ፣ መኖር አለበት፡፡ በጭፈራ በስካር የተሰጠውን ጊዜ ማቃጠል ራስንና እግዚአብሔርን መበደል ከቃለ እግዚአብሔር መኮብለል በኀጢአት ገደል መውደቅ በዚህም እንደታላቅ ሰው መመጻደቅ አይገባም፡፡ ጊዜ መሣሪያ እንጂ መቀለጃ አይደለም፡፡ መጽደቂያ እንጂ መኮነኛ፣ መነሻ እንጂ መውደቂያ፣ መሣሪያ እንጂ መክሰሪያ፣ ሊሆን አልተሰጠም፡፡ ታዲያ በዚህ እንደ አበባ በተሰጠን ጊዜ መጠቀም ድርሻችን ነው፡፡ ስለ አበባ ይህን ያክል በጥቂቱ ካልን፡-

 

ከፍሬስ የምንማረው ምንድር ነው?

አበባው ሲያልፍ ፍሬው ይተካል፡፡ ስለፍሬው ለመነጋገር ከዛፎች መነሣቱ ግልጽ ያደርግልናል፡፡ የአበቦችም የፍሬዎችም ተሸካሚ ወይም አስገኝ ዛፎች ስለሆኑ ያለ ዛፍ ፍሬን ማሰብ ከባል በፊት ልጅ እንደማለት ነውና፡፡ ዕፅዋት፣ አዝርዕት አትክልት ሲያፈሩ በአንድ መንገድ ብቻ አያፈሩም በራሳቸው የሚያፈሩ አሉ፡፡ በጎናቸው የሚያፈሩ አሉ፤ በሥራቸው የሚያፈሩ አሉ፡፡ እነዚህ ሁሉ ምሳሌነት ያላቸው አስተማሪዎች ናቸው በራሳቸው የሚያፈሩት በራሳቸው ጥረው ግረው የሚኖሩ ሰዎች  አምሳል ናቸው፡፡ በጎናቸው የሚያፈሩት ሚስት አግብተው፣ ልጅ ወልደው፣ በሐብታቸው ነግደው፣ በንብረታቸው ተጠቅመው የሚኖሩ ሰዎች አምሳል ናቸው፡፡

 

በሥራቸው የሚያፈሩት ሎሌዎቻቸውን ሠራተኞቻቸውን አዝዘው ልከው የሚኖሩ ሰዎች አምሳል ናቸው ይህ ሰሙ ነው ወርቁ ግን “አንዱ መቶ አንዱ ስልሣ አንዱ ሠላሳ ፍሬ ሰጠ” ማቴ.13፥8-10፡፡

 

በራሳቸው የሚያፈሩት የባለመቶ ክብር አምሳል ናቸው፡፡ በጎናቸው የሚያፈሩት የባለ ሥልሳ ክብር በሥራቸው የሚያፈሩት የባለ ሠላሳ ክብር አምሳል ናቸው፡፡

 

ከነዚህም አዝርዕት፣ ዕፅዋት፣ አትክልት ወገን በራሳቸው በጎናቸው በጫፋቸው አፍርተው ፍሬያቸውን ወፍ ጠርጥሮት፣ ጠላት ለቅሞት የሚቀሩ አሉ፡፡ በሥራቸው አፍርተው ፍሬያቸውን ከወፍ ከጠላት ሰውረው የሚያስቀሩ አሉ እነዚህ ምሳሌዎች ናቸው፡፡

 

በራሳቸው አፍርተው ፍሬያቸውን ወፍ ጠርጥሮት፣ ጠላት ለቅሞት የሚቀሩ በዚህ ዓለም ብዙ ትሩፋት፣ ብዙ ምግባር ሠርተው ይዩልን፣ ይሰሙልን፣ ይወቁልን ብለው በከንቱ ውዳሴ ተጎድተው በወዲያኛው ዓለም ሳይጠቀሙ የሚቀሩ ሰዎች አምሳል ናቸው፡፡

 

በሥራቸው አፍርተው ፍሬያቸውን ከወፍ ከጠላት ሰውረው የሚያስቀሩ በዚህ ዓለም ሲኖሩ ብዙ ትሩፋት ምግባር ሰርተው አብልተው አላበላንም፣ አጠጥተው አላጠጣንም፣ አልብሰው አላለበስንም እያሉ ክብራቸውን ሸሽገው በወዲያኛው ዓለም የሚጠቀሙት አምሳል ናቸው፡፡

 

ዳግመኛም ከአንድ መሬት በቅለው የሚበሉ የማይበሉ፣ የሚጣፍጡ የማይጣፍጡ፣ ሬትና መርዝ፣ ወይንና ትርንጎ ይገኛሉ፡፡ ሬትና መርዝ የኀጥአን፣ ወይንና ትረንጎ የጻድቃን ምሳሌዎች ናቸው፡፡ እነዚህ ከአንድ መሬት በቅለው በመጣፈጥና በመምረር እንዲለዩ ጻድቃንና ኀጥአንም ከአንድ ከአዳም ከአራቱ ባሕርያት ተፈጥረው በምግባርና በሃይማኖት፣ በክህደትና በኀጢአት፣ በክፋትና በበጎነት ተለይተው ሲኖሩ ጻድቃን ወደ ጎተራው መንግሥተ ሰማያት ይገባሉ፡፡ ኀጥአን ግን አይገቡም፡፡ ወደ ገሃነመ እሳት ይወርዳሉ እንጂ፡፡ “ፍሬያቸው ሐሞት ነው፡፡ ዘለዓለም መራራ ነው” እንዲል ዘዳ.32፥33፡፡

 

እነዚህ አዝርዕት፣ አትክልት፣ ዕፅዋት በየዘራቸው ይበቅላሉ እንጂ ያለ ዘራቸው አይበቅሉም፡፡ ፍሬም አይሰጡም፡፡ እንደዚሁም ጻድቃንና ኀጥአንም ያለ ዘራቸው ያለ ቤታቸው አይበቅሉም፡፡

 

“ወእምፍሬሆሙ ተአምርዎሙ እስመ ዕፅ ሠናይ ፍሬ ሰናየ ይፈሪ ወዕኩይሰ ዕፅ ፍሬ እኩየ ይፈሪ” ማቴ.7፥16-18


“ከፍሬአቸው ታውቋቸዋላችሁ መልካም ዛፍ ሁሉ መልካም ፍሬ ያፈራል ክፉ ዛፍም ክፉ ፍሬን ያደርጋል”

 

ከአዝርዕት ከአትክልት ክረምት ለምልመው በጋ የሚደርቁ ክረምት ደርቀው በበጋ የሚለመልሙ አሉ፡፡ በክረምት ለምልመው በበጋ የሚደርቁት በዚህ ዓለም ሳሉ በልተው፣ ጠጥተው፣ ለብሰው፣ ሞግሰው በዚያኛው ዓለም የማይጠቀሙት ናቸው፡፡ እንደነዌ ያሉ ሉቃ.16፥25

 

ክረምት ደርቀው በጋ የሚለመለሙት በዚህ ዓለም ሲኖሩ ተርበው ታርዘው ጎስቁለው በወዲያኛው ዓለም የሚጠቀሙ ሰዎች አምሳል ናቸው፡፡ እንደ አልዓዛር እንደ ኢዮብ ያሉ ናቸው፡፡ ኢዮ.2፥1፣ ሉቃ.16፥19 ስለዚህ እኛም የሰው ልጆች መራራ ሳይሆን ጣፋጭ፣ ጠላት የሚለቅመው ሳይሆን፣ ከጠላት የሚሰውረውን ፍሬ፣ ክረምት ለምለሞ በጋ የሚደርውን ሳይሆን ክረምት ደርቀው በጋ የሚለመልሙትን መሆን አለብን፡፡

 

እግዚአብሔር በቸርነቱ በምሕረቱ ይርዳን፡፡

ይቆየን