የቃለ ዓዋዲው ማሻሻያ ረቂቅ ይመከርበት!

መስከረም 30 ቀን 2005

ሰበካ ጉባኤ በካህናትና በምእመናን ኅብረት ላይ የቆመ መሠረታዊ የቤተ ክርስቲያናችን አስተዳደራዊና መዋቅራዊ ሥርዐት ነው፡፡ ከመንበረ ፓትርያርክ እስከ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ባሉት መንፈሳዊና አስተዳደራዊ ጉዳዮች ላይ በየደረጃው አመራር ይሰጣል፣

 

ዕቅድ ያወጣል፣ ውሳኔ ያሳልፋል፡፡ ጉባኤው ቤተ ክርስቲያናችን ከመሬት ስሪት ተነሥታ በሕዝብ ባለቤትነት ላይ የተመሠረተችበትና ሕጋዊ ሰውነት ያገኘችበትም የሕግ አካል ነው፡፡

 

በየደረጃው በሚያወጣቸው ዕቅዶች፣ በሚሰጣቸው አመራርና በሚያሳልፋቸው ውሳኔዎቹ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ይጠብቃል፡፡ አገልግሎቷንም የተሟላ እንዲሆን ያደርጋል፡፡ የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች በሐዋርያዊ ተግባር እንዲደራጁ በማድረግ ችሎታቸውን ተጠቅሞ ኑሮአቸውን ያሻሽላል፡፡ ምእመናንን ለማብዛትና በመንፈሳዊ ዕውቀት ጎልምሰው በምግባርና በሃይማኖት ጸንተው በክርስቲያናዊ ሕይወት እንዲኖሩ ያደርጋል፡፡

 

እነዚህን ዓላማዎቹን ከማስፈጸም አኳያ ጾታ ካህናትና ጾታ ምእመናን /ጳጳሳት፣ ቀሳውስት፣ ሊቃውንት፣ ወጣቶች/ በምልዐት የተወከሉበትም በመሆኑ አሳታፊ ነው፡፡

 

ይሁንና በአጥቢያ ሰበካ ጉባኤ ደረጃ የምእመናን ንቃተ ሕሊና እየዳበረ ቢሆንም ተሳትፎው በሚፈለገው ደረጃ እያደገ አይደለም፡፡ ሰበካ ጉባኤ በወረዳ ቤተ ክህነትና በመንበረ ጵጵስና አካባቢ የተረሳም ይመስላል፡፡ በየዓመቱ የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ቢካሔድም፤ በጉባኤውም አልፎ አልፎ ሥልጠናዎች መስጠታቸው ቢበረታቱም ወደ መሬት የማይወርዱ ወደ ተግባር የማይለወጡ መሆናቸውን እንረዳለን፡፡

 

ዘንድሮም ከጥቅምት 6-11 ቀን 2005 ዓ.ም ጀምሮ ሠላሳ አንደኛው የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ በጽርሐ መንበረ ፓትርያርክ ይካሔዳል፡፡ እናም ተገቢ /የካህናት፣ የወጣቶችና የምእመናን/ የውክልና ተሳትፎው እንዲጠበቅ፣ ከተለመደው ሪፖርታዊ መግለጫ በዘለለ ቁም ነገራዊ አጀንዳ ተኮር ቢሆን፤ አጀንዳዎቹ በወቅታዊና ዘላቂ በሆኑ ጉዳዮች ላይ ያተኮሩ፣ አወያይና አሳታፊ ሊሆኑ ይገባል እንላለን፡፡

 

ከሪፖርት አቀራረብ ጋር በተያያዘም የአህጉረ ስብከት ሪፖርት በጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ ተጠቃሎ ቢቀርብና የቁጥጥር አገልግሎት ሪፖርት ተጠያቂነትንና ግልጽነትን ከማስፈን አኳያ ራሱን ችሎና ለብቻው ተለይቶ ቢቀርብና ተገቢ የሆነ ውይይትም ሊደረግበት ይገባል፡፡

 

በዘንድሮው የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ በቃለ ዐዋዲው ማሻሻያ ረቂቅ፣ ተቋማዊ ማሻሻያ (Structural Reform)፣ በዕርቀ ሰላሙ እውንነት ላይ፣ በፓትርያርክ ምርጫ አፈጻጸም ሥርዐት ላይ አተኩሮ እንዲወያይና የውሳኔ አሳብ ለቅዱስ ሲኖዶስ እንዲያሳልፍ ቢደረግ፤ ከአምስተኛው ፓትርያርክ ዕረፍት በኋላ ቤተ ክርስቲያኒቱ ያለችበትን ነባራዊ ሁኔታ የሚያሳይና በቀጣይነት ሊደረጉ የሚገባቸውን የሚጠቁም ሰነድ በዐቃቤ መንበሩ የሚመራው ኮሚቴ አዘጋጅቶ የጉባኤው ተሳታፊ እንዲወያይበት ሊደረግ ይገባል፡፡ ጉባኤው ዕቅድና በጀት መትከል ቢጀምር፣ የክትትልና ቁጥጥር ሥልትን አቅጣጫ ቢበይን ለቤተ ክርስቲያን ሁለንተናዊ ዕድገት ጠቃሚ መሆኑን እናምናለን፡፡

 

ሌላው ቢቀር እንኳን የቃለ ዓዋዲው ማሻሻያዎች ላይ የመንበረ ፓትርያርክ ሠላሳ አንደኛ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ተሳታፊዎች እንዲመክሩበትና እንዲያዳብሩት ዕድሉ ሊሰጣቸው ይገባል፡፡

 

ይህን ስንል የቃለ ዓዋዲው መሻሻል የአሁኑንና የቀጣዩን ዘመን የቤተ ክርስቲያናችንን ሐዋርያዊ አገልግሎት፣ ርምጃ ለማስቀጠል የላቀ አዎንታዊ ተፅዕኖ ያለው መሆኑን በመገንዘብ ነው፡፡

 

በዚህ መልኩ የቃለ ዓዋዲው መሻሻል ተግባራዊ መሆን ለመዋቅር ማሻሻያችን መርሕ ይሆናል፤ የሕግ አውጪውን፣ ሕግ አስፈጻሚውንና የሕግ ተርጓሚውን ተግባር፣ ሥልጣንና ሓላፊነት በመለየት፡-

 

  • ተጠያቂነትና ግልጽነት እንዲሰፍን፣
  • የቤተ ክርስቲያናችን ሀብት /የሰው ኀይል፣ የገንዘብና ንብረት/ በአግባቡ ጥቅም ላይ እንዲውል፣
  • ቤተ ክርስቲያናችን በመንፈሳዊነት ምሳሌያዊ የሆነችና ሞራላዊ የበላይነት ያላት ተቋም እንድትሆን /በብኩንነት፣ ምዝበራና ዘረፋ ላይ/ ያስችላታል፡፡

 

በዓለም አቀፍም ደረጃ /በውጭው ዓለም/ ላለችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንም የበለጠ የመስፋፋትና የአንድነት በርን ይከፍታል እንላለን፡፡

 

ስለዚህ የዘንድሮ የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ በቃለ ዓዋዲው ማሻሻያ ላይ ለመምከር ባለቤትም፣ ባለሥልጣንም ነውና ይመለከተዋል፡፡ አሁን ባለንበት ሁኔታ ከዚህም የተለየ፣ ከዚህም የበለጠ አጀንዳ ሊኖረው አይገባም፡፡ ቢያንስ ቢያንስ በቃለ ዐዋዲው ማሻሻያዎች ላይ ይምከር! ማሻሻያዎቹን ያዳብር! እንላለን፡፡

 

  • ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 20ኛ ዓመት ቁጥር 2  ከጥቅምት 1-15 ቀን 2005 ዓ.ም.

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ዘመነ ጽጌ

ginbote 26 035

በ44ቱ የሀገር ውስጥ ማእከላት ጠቅላላ ጉባኤ ይደረጋል

መስከረም 28 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደጀኔ

 

ማኅበረ ቅዱሳን በሀገር ውስጥ አገልግሎቱን ለማፋጠን ባቋቋማቸው 44 ማእከላት ጠቅላላ ጉባኤ እንደሚያካሂድ ተገለጸ፡፡

ginbote 26 035የሀገር ውስጥ ማእከላትና የግቢ ጉባኤያት ማደራጃና ማስተባበሪያ ዋና ክፍል ሓላፊና ምክትል ዋና ጸሓፊ ዲ/ን አንዱአምላክ ይበልጣል እንደገለጹት ማእከላት ጠቅላላ ጉባኤያቸውን ከጥቅምት 15 እስከ ኅዳር 2 ቀን 2005 ዓ.ም. እንደሚያደርጉ ገልጸዋል፡፡

ጠቅላላ ጉባኤ በዚህ ወቅት እንዲደረግ ምክንያቱ የማኅበሩ ቀጣይ የ4 ዓመት ስልታዊ ዕቅድ በማኅበሩ 10ኛ ጠቅላላ ጉባኤ ማጽደቅ ስለነበረበት መሆኑን ገልጸው ማእከላቱም የቀጣይ 4 ዓመት ዕቅዳቸው በስልታዊ ዕቅድ መሠረት የሚያዘጋጁ ሲሆን የ2005 ዕቅዳቸውም በጉባኤው የሚጸድቅ በመሆኑ ነው፡፡

 

ከጥቅምት አጋማሽ እስከ ኅዳር መባቻ ድረስ በሚደረገው ጉባኤም በየማእከላቱ ከዋናው ማእከል ተወካይ ልዑክ የሚገኝ ሲሆን በጉባኤውም የ2004 ዓ.ም. የዕቅድ አፈጻጸምና የኦዲት ሪፖርት ቀርቦ ይገመገማል የተለያየ አጀንዳም ቀርቦ ውይይት የሚደረግበት ሲሆን ጉባኤውም የ2005 ዓ.ም. ዕቅድ በማጽደቅና የአገልግሎት ጊዜያቸውን የፈጸሙ የማእከላት የሥራ አስፈጻሚ ጉባኤ ምርጫ ይካሄዳል፡፡

 

በጠቅላላ ጉባኤውም የማእከላቱ አባላት፣ የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ፣ የሀገረ ስብከት ሓላፊዎች፣ የሰበካ ጉባኤና የሰንበት ትምህርት ቤቶች ተወካዮች፣ የምእመናን ተወካዮች፣ የወረዳ ማእከላትና የግንኙነት ጣቢያዎች ተወካዮች ይሳተፋሉ፡፡

 

በዚህ የማእከላት ጠቅላላ ጉባኤ እያንዳንዱ ማእከል ለ2 ቀናት የሚቆይ ጉባኤ የሚያደርግ መሆኑን የገለጹት ዲ/ን አንዱ አምላክ ይበልጣል ከማእከላቱ ጠቅላላ ጉባኤ በመቀጠልም በማእከላቱ ስር የሚገኙ ወረዳ ማእከላት ጠቅላላ ጉባኤያቸው የሚያከናውኑ መሆኑን አስረድተዋል፡፡

 

ማኅበረ ቅዱሳን በአሁኑ ወቅት መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎቱን ለማሳለጥ በሀገር ውስጥ ብቻ 44 ማእከላት፣ 333 ወረዳ ማእከላት 183 ግንኙነት ጣቢያዎችና 325 የግቢ ጉባኤያትን ያዋቀረ መሆኑ ይታወቃል፡፡

meskel 1

መስቀል (ለሕፃናት)

መስከረም 22 ቀን 2005 ዓ.ም


ቢኒያም ፍቅረ ማርያም


meskel 1እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች? እግዚአብሔር ይመስገን፡፡ እንኳን ከዘመነ ዮሐንስ ወደ ዘመነ ማቴዎስ በሰላም አሸጋገራችሁ፡፡ ትምህርት ቤት ተከፍቶ በአዲስ ደብተር፣ በአዲስ እስክርቢቶ፣ በአዲስ ልብስ … ስትማሩ ምን ተሰማችሁ? በጣም ያስደስታል አይደል? ይህ ሁሉ የሆነው እግዚአብሔር አዲስ ዘመን አዲስ ዓመት ስለሰጠን ነው፡፡ መስከረም 17 የሚከበረው የመስቀል በዓልም የእግዚአብሔር ሥጦታ ነው፡፡

 

የዘወትር ጸሎት በሚጸለይበት ጊዜ ስለመስቀል እንዲህ የሚል አልሰማችሁም “…መስቀል ኀይላችን ነው፤ ኀይላችን መስቀል ነው፤ የሚያጸናን መስቀል ነው፤ መስቀል ቤዛችን ነው፤ መስቀል የነፍሳችን መዳኛ ነው፡፡ አይሁድ ይክዱታል እኛ ግን እናምነዋለን፡፡ ያመንነው እኛ በመስቀሉ እንድናለን፡፡ ድነናልም፡፡ …” እያልን የምንጸልየው እኛ በጉልበታችን፣ በእውቀታችን ባለን ነገር ሁሉ እንዳንመካ፤ ነገር ግን በመስቀሉ እንድንመካ ነው፡፡

 

በመስቀል እንመካለን ምክንያቱም መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከጥንት ጀምሮ ማለትም ከአባታችን አዳም ከእናታችን ሔዋን ጀምሮ እስከ አሁን ጠላታችን የሆነው ዲያብሎስን እንደ ደካማ በመስቀል ተሰቅሎ /ተቸንክሮ/ ድል ስላደረገው፤ አዳምና ሔዋንን ከሲዖል እስራት ነፃ ስላደረጋቸው ነው፡፡ ለእኛም መስቀሉ መመኪያችን ሆኖ ዲያብሎስ መስቀሉን ሲያይ ይሸሸናልና ነው፡፡

 

ልጆች መስከረም 17 የምናከብረው የመስቀል ደመራ በዓል ምክንያት አይሁድ መስቀሉ የታመሙትን እንደሚፈውስ፣ የሞቱትን እንደሚያስነሣ ባወቁ ጊዜ በክፉ ቅናት ተነሣሥተው በመስቀሉ ክብር እንዳይገኝ ቆፍረው ቀብረውት፣ ቆሻሻ መጣያም አድርገውት ስለነበር እግዚአብሔርም መስቀሉ ተቀብሮ እንዲቀር ስላልፈለገ ንግሥት እሌኒን አስነሥቶ አባ መቃርስ እና አባ ኪራኮስ በሚባሉ አባቶች መሪነት በቦታው በደረሱ ጊዜ ቦታው ከቆሻሻው ክምር የተነሣ ተራራ ሆኖ ስለነበር ትክክለኛው ቦታ የት እንደሆነ ማወቅ አልቻሉም፡፡

 

ንግሥት እሌኒም ወደ እግዚአብሔር በመጸለይዋ የእግዚአብሔር መልአክ ተገልጦላት ደመራ እንድትደምር በዚያም ላይ እጣን እንድትጨምር ስለነገራት አገልጋዮቿን ወታደሮቿን ጠርታ በአካባቢው ደመራ እንዲተክሉ፣ እንዲያቀጣጥሉ፣ እጣንም እንዲጨምሩበት ነገረቻቸው፡፡ በተባሉትም መሠረት አድርገው ጢሱ  ወደሰማይ ከወጣ በኋላ በእግዚአብሔር ኀይል ተመልሶ መስቀሉ ወደ ተቀበረበት ተራራ አመለከተ፡፡ በዚህ ጊዜ ንግሥት እሌኒ እና አገልጋዮቿ ደስ አላቸው፡፡

 

ከስድስት ወራት ቁፋሮ በኋላ ሦስት መስቀሎች ተገኙ፡፡ የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ መስቀልም የታመሙትን ሲፈውስ ሙት ሲያስነሣ በማየታቸው ከሁለቱ መስቀሎች ለመለየት ችለዋል፡፡ ዲያብሎስ በአይሁድ ላይ አድሮ መስቀሉን ቢደብቅም በእግዚአብሔር ኀይል ሊገኝ ችሏል፡፡ ልጆች መስቀላችሁን አትደብቁ እሺ! ቸር ሰንብቱ፡፡

ለቤተ ክርስቲያናችን አንድነት ዕርቅና ሰላም መሠረት ናቸው

መስከረም 22 ቀን 2005 ዓ.ም.


የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በየዘመኑ የተለያዩ ፈተናዎች የተፈራረቁባት ሲሆን ቤተ ክርስቲያኒቱ የእግዚአብሔር ማደሪያ ነችና የመጣውን የፈተና ጎርፍና ነፋስ ሁሉ ተቋቁማ አሁን ላለንበት ዘመን ደርሳለች፡፡ የዐላውያን ገዢዎችን ሰይፍ ከውስጥም ከውጭም የነበሩ መናፍቃንን ቅሰጣ ተሻግራ እስከአሁን የሐዋርያትን፣ የቅዱሳን ሊቃውንትን የአትናቴዎስን የቄርሎስን ሃይማኖት ይዛ ተገኝታለች፡፡፡ ስለዚህም ቤተ ክርስቲያን የሚመጡባትን ፈተናዎች የምታደንቅ፣ በዚያም ተስፋ የምትቆርጥ አይደለችም፡፡ ሁል ጊዜም ቢሆን የገሃነም ደጆች የሚሰብቁት ግልጽና ስውር ጦር እንዳለ ስለምታውቅ ከሚመጣው ፈተና ሁሉ አሸንፋ ትወጣ ዘንድ ወደ አምላኳ ትለምናለች እንጂ፡፡

 

በዚህ ባለንበትም ዘመን ቤተ ክርስቲያናችን ካጋጠሟት ከባድ ፈተናዎች አንዱ ለሃያ ዓመታት ያህል የቆየው የአባቶች መለያየት ጉዳይ ነው፡፡ እንዲህ ያሉ ታሪኮች በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ውስጥ እንግዳ ነገር ባይሆኑም የሚያስከትሉት ጉዳት ግን ቀላል የማይባል ነው፡፡ በማወቅም ባለማወቅም ከውስጥ ወይም ከውጪ በሆኑ ምክንያቶች እንዲህ ያሉ መለያየቶች ሊከሰቱ ይችላሉ፡፡ ዋናው ነጥብ ግን ከርስትና በሃይማኖት ምክንያት ካልሆነ በቀር ለመለያየት፣ መንጋን ለመበተን ወይም ለመከፋፈል የሚያበቃ ሥነ ኅሊና /ሞራል/ የሚሰጥ ሃይማኖት አይደለም፡፡ ሃይማኖታችን ተስፋ እንድናደርግ የሚነግረንን የእግዚአብሔር ጸጋ ሁሉ መንግሥቱንም ማግኘት የሚቻለው የዕርቅና ሰላም ሕይወት ሲኖረን ነው፡፡ ጌታችን “እኔ እንደወደድኳችሁ እርስ በእርሳችሁ ትዋደዱ ዘንድ ትእዛዜ ይህች ናት” እንዳለ የሕጉ ሁሉ ፍጻሜ ነው፡፡ /ዮሐ.15፥12/ እርስ በእርስ ብቻም ሳይሆን ብንችል ከሁሉም ጋር በሰላም እንድንኖር ታዘናል፡፡ ያለሰላምና ፍቅር ቤተ ክርብስቲያንን ማነጽ ማጽናትም አይቻልም፡፡

 

በ1983 ዓ.ም. ጀምሮ ቤተ ክርስቲያናችን ያጋጠማት መከፋፈል ከግብጽ ቤተ ክርስቲያን ሞግዚት አስተዳደር ነጻ ወጥተን እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ በተመሠረተው መንበረ ፓትርያርክ ጥንካሬ እና አሠራር ላይ ጥያቄም የሚያስነሣ ሆኗል፡፡ በቤተ ክርስቲያን የውጪና የሀገር ውስጥ የአገልግሎት እንቅስቃሴዎችም ላይ ተፅዕኖ ማሳደሩ አልቀረም፡፡ ቤተ ክርስቲያን የሲኖዶሱ፣ የስደተኛው፣ የገለልተኛው ወዘተ እየተባለች ሁሉም እንደፈቃዱ የሚኖርባት ሆና ቆይታለች፡፡

 

እነዚህ ነገሮች ዕረፍት የነሧቸው የተለያዩ ወገኖችም በአባቶች መካከል ያሉ ችግሮች እንዲፈቱ የተለያዩ ጥረቶች ሲያደርጉ ቆይተዋል፡፡ ይሁን እንጂ ችግሮቹ እልባት አግኝተው ቤተ ክርስቲያኒቱ ወደቀድሞው አንድነቷ ሳትመለስ በሂደት ላይ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ዐረፉ፡፡ የእርሳቸው ዕረፍትን ተከትሎም ችግሮቹ የበለጠ እንዳይወሳሰቡና መቋጫ ሳያገኙ ወደባሰ ቀውስ፣ አለመረጋጋትና ማባሪያ ወደሌለው መወጋገዝ እንዳይገባ እስከቀጣዩ ፓትርያርክ ሢመት ድረስ አስፈላጊውን ሁሉ ጥረት ከመቼው ጊዜ በላቀ ሁኔታ እንዲቀጥል ብፁዓን አባቶችን ጨምሮ ሁሉም ወገን ግፊት እያደረገ ነው፡፡

 

አገልግሎቱን አጠናክሮ የቤተ ክርስቲያኒቱን መልካም ነገር ሁሉ ማየት ዋነኛ ግቡ የሆነው ማኅበረ ቅዱሳንም የቤተ ክርስቲያናችን አንድነት ጉዳይ በእጅጉ ያሳስበዋል፡፡ መለያየቱ በሚሰጠው አገልግሎት ላይ ከፍተኛ ጫና ማሳደሩን በተጨባጭ ያየው ማኅበረ ቅዱሳን ለሁሉም የቤተ ክርስቲያን የአገልግሎት ቤተሰቦች ጉዳዩ አንገብጋቢ መሆኑን ይረዳል፡፡

 

በዚህ መለያየት ውስጥ ዓላማቸውን ለመፈጸም ይጥሩ የነበሩ ግለሰቦችና ቡድኖች በቤተ ክርስቲያናችን መዋቅር ውስጥ ለመንሰራፋትም ይውተረተሩ እንደነበር ይታወቃል፡፡ አገልግሎታችንም በሚፈለገው ደረጃ በፍጥነት ሄዷል ማለት አይቻልም፡፡ በርካታ ምእመናን በመናፍቃን ተወስደዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያን የሚፈለገውንም ያህል ሀገራዊ አስተዋጽኦ ስታደርግ ቆይታለች ለማለት አያስደፍርም፡፡

 

ሌሎች ምክንያቶችም እንዳሉ ሆነው ይኸው በአባቶች መካከል ያለው መለያየትም ከላይ ለዘረዘርናቸው ውስንነቶች የራሱ አስተዋጽኦ ነበረው፡፡ መንበረ ፓትርያርክና ቅዱስ ሲኖዶስ ከአንድ ሺሕ ስድስት መቶ ዓመታት በኋላ ከግብጽ ቤተ ክርስቲያን አስተዳደራዊ ቁጥጥር ተላቀው ያገኙትን መንፈሳዊ ሥልጣንና መንበር በተሻለ አሠራር ወደላቀ የአገልግሎት አቅም የሚያደርሱበትን ሁነኛ ጊዜዎች በእነዚህ መለያየቶች ምክንያት አባክነዋል ማለት ይቻላል፡፡ የተሻለ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት መስፋፋት ማሳየት ሲቻል ወደ ኋላ ለመመለሱ አስተዋጾኦ አድርጓል፡፡ ይህ በሁሉም ልብ ያለ ሐዘን እንዲቀረፍ አባቶች ጥረት ሲያደርጉ ቢቆዩም በቀላሉ ተፈቶ ቤተ ክርስቲያንን አንድ ማድረግ ሳንችል መዘግየታችን ትውልዳችንንም የሚያስወቅስ ሆኗል፡፡

 

ይሁን እንጂ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ በሕይወት እያሉ ተጀምሮ የነበረው የዕርቅና ሰላም ሂደት አሁን እልባት እንዲሰጠው የሚያስገድድ ሁኔታ ውስጥ መግባታችንን ማኅበረ ቅዱሳን ያምናል፡፡ ማኅበራችን የዕርቅና ሰላሙ ጉዳይ አስተዳደራዊ ጉዳይ ብቻም ሳይሆን የክርስቲያናዊ ሕይወትና ሥነ ምግባር ጉዳይ መሆኑ እንዲታሰብበት ይሻል፡፡ ስለዚህ አፋጣኝ እርምጃ መውሰድና ችግሩን ለመፍታት በሚያሳምን ደረጃ መንቀሳቀስ ይጠይቃል፡፡ ጉዳዩም ክብደት እንዲሰጠው ይፈልጋል፡፡ የምናገለግላት ቤተ ክርስቲያን በየምክንያቱ እየተለያየች ባለብዙ መዋቅር ስትሆን ማየት የማይታገሱት ነገር ነው፡፡ የዕርቅና የሰላም ሂደቶቹም ውጤት በግልጽ እየቀረቡ ሕዝበ ክርስቲያኑም ግፊት እንዲየደርግባቸው ይሻል፡፡

 

ለዚህም በደሙ የዋጃትን ቤተ ክርስቲያን እንዲጠብቁ ለመንጋውም እንዲጠነቀቁ አደራ የተሰጣቸው ብፁዓን አባቶች ድርሻ የጎላ ነው፡፡ ዕርቅና ሰላምን በቤተ ክርስቲያን አስፍኖ የቤተ ክርስቲያንን አንድነት ማጽናት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ለአገልግሎት የሚመች ስልታዊ አካሄድ አሠራርና አደረጃጀት እንዲሰፍን መፍቀድ ይጠበቅባቸዋል፡፡ ይህንንም ከእግዚአብሔር የሆነውን አደራ ከመጠበቅ አንጻር፣ ለአገልግሎቱ ስኬት ከማምጣት፣ ምእመናን በአገልግሎቱ ረክተው እንዲጸኑ ከማድረግ፣ በታሪክ ውስጥ ተጠያቂ ካለመሆን አንጻር ሁሉ ሓላፊነትን ሊወጡ ይገባል፡፡

 

ሁሉም የክርስቲያን ወገን ቢሆን ሊረዳው የሚገባው የሰበሰበችን ቤተ ክርስቲያን እጅግ ታሪካዊ ባዕለጸጋና አኩሪ መሆኗን ነው፡፡ የሊቃውንቱ የቅዱስ ያሬድ የአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ፣ የእነ አቡነ ተክለሃይማኖት የእነ አቡነ ኤዎስጣቴዎስ ቤተ ክርስቲያን መሆኗን ልንረዳ ይገባል፡፡ ብዙ ዋጋ ተከፍሎባታል፡፡ ስለዚህ ክብርና አንድነቷን ዕርቅና ሰላምን በማስፈን ልናጸና ይገባል፡፡ ላለብን ችግር መፍትሔ የሚሰጠውም ፈጣሪ መሆኑን በማመን ብፁዓን አባቶችን በጸሎት መርዳት ይገባል፡፡ የቤተ ክርስቲያኒቱን አንድነት በጥብቅ እንደምንፈልገውም በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ መግለጽ ግፊትም ማድረግ ይገባናል፡፡ ለሚፈለገው አንድነት ደግሞ መሠረቱ ዕርቅና ሰላም ነው፡፡

 

ቤተ ክህነቱም እግዚአብሔር ያለፈውን ይቅር እንዲለን፣ ከሚመጣውም እንዲጠብቀን ስለ አንድነታችን በጸሎት ሊተጋ ይገባል፡፡ ያለፈው መልካም ያልሆነው ነገር ሁሉ ሊረሳ፣ በጎው ደግሞ ሊወሳ ይገባል፡፡ በጎ ፈቃድና ሰላምን መውደድ ከሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስ የተማርነው የተረዳነው ነውና ሁሉም ወገን ያንኑ እንዲያጸና መምከር ይጠበቅበታል፡፡

 

ማኅበረ ቅዱሳንም በበኩሉ ከዚህ ቀደም ይዞት የቆየውን ይህንኑ አቋም አሁንም ለማስተጋባት የተገደደው ከችግሩ ወቅታዊነትና ከጊዜው አንገብጋቢነት የተነሣ ነው፡፡ ስለዚህ ችግሩ ከምንም ዓይነት መዘዝ በጸዳ ሁኔታ፣ ቀኖናዊና ሃይማኖታዊ መሠረቶች ተጠብቀው ዕርቅና ሰላምን የማስፈን እንቅስቃሴው በሚያሳምን ደረጃ ሊኬድበት ይገባል፡፡ የአባቶችና የሀገር ሽማግሌዎችም ጥረት ሊመሰገን እንደሚገባው ማኅበረ ቅዱሳን ያምናል፡፡ ውጤት እስከሚገኝ ለሂደቱ አስፈላጊውን ሁሉ አስተዋጽኦ ሊያበረክት መዘጋጀቱን ለሁሉም ወገን ሊገልጽ ይወዳል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

  • ምንጭ፡- ሐመር መጽሔት 20ኛ ዓመት ቁጥር 5 2005 ዓ.ም.

ማኅበረ ቅዱሳን ትእምርተ ሰላም

መስከረም 21 ቀን 2005 ዓ.ም.


በኢትዮጵያ ከጥቂት ዓመታት ወዲህ ከሃይማኖት አክራሪነት ጋር በተያያዘ አንዳንድ ግጭቶች መከሰታቸው ይታወቃል፡፡ መንግሥትም ለችግሩ  መፍትሔ ለመስጠት ጥረት እያደረገ ይገኛል፡፡ የአብዛኛዎቹ የ”ግጭት” ጠባይ ግን የተለየ ነበር፡፡ የሁለት እምነት ተከታዮች በመፎካከርና በመወዳደር ወይም ደግሞ ከተራ ጥላቻና ግለሰባዊ ግጭት አንሥተው ሃይማኖታዊ ያደረጉት አልነበረም፡፡

 

ከዚያ ይልቅ በአንድ ወገን ያሉት በማያውቁትና ባላሰቡት ሰዓት የደረሰ ድንገተኛ አደጋ ነበር ማለት ይቻላል፡፡ ጥቃቱን የፈጸሙትም የሚከተሉትን ሃይማኖት አባቶች ወካዮችና ከዚያው ከቤተ እምነታቸው ተከታዮች ሙሉ ይሁንታ አግኝተው የተላኩ አልነበሩም፡፡ ይህን የማድረግ ዓላማ ብቻ ሳይሆን በቂ ዝግጅትና ጥናት ያደረጉ የሃይማኖት አክራሪዎች መሆናቸው ከድርጊታቸውም፤ ከተገኘውም ማስረጃ ግልጽ ነበር፡፡

 

በተከታታይ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ምእምናንና አብያተ ክርስቲያናት ላይ በአርሲ ዞን ቆሬ ወረዳ በአንሻ ቀበሌ፣ በጅማና ኢሉአባቦራ ጥቃት ሲያደርስ የነበረው የአክራሪ እስልምና ቡድን ኢትዮጵያዊ መልኩን አሽቀንጥሮ ጥሎ እስላማዊ ዓለም ዓቀፋዊ ግዛትን ለማፋጠንና የምሥራቅ አፍሪካ ስልቱን ለመፈጸም እንደመሰናክል ያያትን የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን ለማስወገድ ያለመው እንቅስቃሴው አካል እንደነበረም እንገነዘባለን፡፡

 

ይህን ተከትሎም በሕዝቡ መካከል ለዘመናት አብሮ የመኖር ባህላችንን የሚፃረር ድርጊት እየተስተዋለ ነበር፡፡ በተለይ ደግሞ በክርስቲያኑና በሙስሊሙ ማኅበረሰብ መካከል በወቅቱ ተፈጥረው የነበሩት አዳዲስ ክስተቶች በሁለቱ ሃይማኖት ተከታዮች መካከል የማያባሩና መቆሚያ የሌላቸው ግጭቶች መፍጠር ዓላማ አድርገው የሚንቀሳቀሱ ባዕዳን ኀይሎች በአምሳላቸው የወለዷቸው አክራሪዎች የሚመሩት እኩይ ድርጊት መሆኑም ድርስ ነበር፡፡ ከጥቃቱ በኋላም መንግሥት ተገቢውን ትኩረት በመስጠት የተለያዩ የማስተማርና ሕግ የማስከበር ሥራዎችንም ሲሠራ እንደነበረም በሚገባ እናውቃለን፡፡

 

ትናንትም ሆነ ዛሬ ምልክቱ ሰላም እንጂ “አክራሪነት” ያልሆነው ማኅበረ ቅዱሳን ሀገራዊ ድርሻውን በሦስት መልኩ ተወጥቷል፡፡ የመጀመሪያው ከመጀመሪያው ጀምሮ ምእመናን አክራሪውን፣ ነባሩንና ሰላማዊውን እስልምና ነጥለው እንዲመለከቱ ከፍተኛውን ድርሻ ተወጥቷል፡፡ ሁለተኛ አክራሪዎቹ ለሚያነሷቸው ታሪካዊና ዶግማዊ ጥያቄዎች በተጻፉት ጽሑፎች መጠንና ቁጥር ጋር ሊነጻጸር ቀርቶ እዚህ ግባ የሚባል ባይሆንም መጠነኛ ምላሾችን ሰጥቷል፡፡ ሦስተኛ ተቻችሎና ተከባብሮ ስለመኖር ከየትኛውም አካል በፊትና በከፍተኛ ሽፋን ሠርቷል፡፡ ስለ አክራሪ እስልምናና ስለትንኮሳው እጅግ አነስተኛና ክስተት ተኮር የሆኑ መረጃዎችን በመስጠት ችግሩ ሲያጋጥም ለመንግሥት ማመልከት እንደሚገባ አቅጣጫ ለማሳየት ሞክሯል፡፡

 

ማኅበሩ ይህን በወቅቱ ያደረገው አንድን ነገር እየሰሙ እንዳልሰሙና እንደሌለ ከመቁጠር ይልቅ ችግሩን በትክክል አሳውቆ ለመፍትሔው መሥራት ይገባል ብሎ ስለሚያምንና መንግሥት በወቅቱ አክራሪነትን ለመግታትና ግጭቶችን ለማስወገድ እያደረገ የነበረውንም ጥረት የማገዝ ሀገራዊ ግዴታንም ከመወጣት አንጻር መሆኑንም ለመግለጽ እንወዳለን፡፡

 

ይሁንና ለቤተ ክርሰቲያኒቱ ተጨማሪ አስተዋጽኦ አበረክታለሁ ብሎ የተደራጀውንና ከሰላማዊ ባሕርይው በመነጨ የሃይማኖት አክራሪነት በጽናትና በአቋም እየታገለ ያለውን ማኅበረ ቅዱሳንን በተሳሳተ መረጃ በአክራሪነት የመፈረጅ አዝማሚያዎች በአንዳንድ አካላት እየታዩ መሆናቸውንም እንረዳለን፡፡

 

በማያወላዳ ሁኔታ ማኅበረ ቅዱሳን ትናንትም ሆነ ዛሬ የሃይማኖት አክራሪ አለመሆኑንና ማንንም ወደ ሃይማኖት አክራሪነት የሚመራ ተቋም አለመሆኑን ለመግለጽ እንወዳለን፡፡ የሃይማኖት ሥርዓታችንን አጥብቀን በመፈጸማችን እንታወቅ ይሆናል እንጂ የአክራሪነት ውጤት በሆኑት ጸብና ግጭት አንታወቅም፡፡ ያለ ስም ስም መስጠትና በተሳሳተ መረጃ መፈረጁ አንዳች መፍትሔ ሊሰጠው እንደሚገባ በጽኑ እናምናለን፡፡

 

ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሃይማኖት አክራሪነትን አስመልክተው ለምክር ቤቱ አባላት ሲገልጹ ከሕዝብና ቤት ቆጠራ ውጤት ጋር አያይዘው “….አንዳንድ የማኅበረ ቅዱሳን አባላት….” ብለው መጥራታቸውን እንደምቹ አጋጣሚ የወሰዱ የማኅበሩን አገልግሎት የማይወዱና ምናልባትም ማኅበሩ ባይኖር በቤተ ክርስቲያኒቱ መሠረተ እምነት፤ ሥርዓተ አምልኮና ትውፊት ላይ የፈለጉትን ማድረግ የሚቻላቸው የሚመስላቸው አካላት የማኅበሩን ስም ማጥፋታቸውን እንደቀጠሉ ናቸው፡፡

 

እነዚህ ወቅታዊ ፓለቲካዊ ሁኔታዎችን የሚንተራሱ የተሐድሶ መናፍቃን አቀንቃኞች ከዚህ በፊት ከቅዱስ ሲኖዶስ ጋር ለማጣለት፣ ከሌሎችም አካላት ጋር በማጋጨት እየደከሙ ሳይሳካላቸው ሲቀር ደግሞ የወቅቱን የፓለቲካ ነፋስ ተጠቅመው መንግሥታዊ አካላትን በማሳሳት በማኅበረ ቅዱሳን መቃብር ላይ ቆመው ቅዠታቸው እውን ሆኖ ለማየት ሲባዝኑ እያስተዋልንም ነው፡፡ ስለዚህም መንግሥታዊ አካላት በእነዚህ አካላት በደረሳቸው የተሳሳተ መረጃ ተመሥርተው ማኅበሩን ከመፈረጃቸው በፊት በቂ ጥናትና አስፈላጊውን ጥንቃቄ እንደሚያደርጉም እምነታችን ነው፡፡

 

ማኅበረ ቅዱሳን በግልጽና በይፋ ከሚሠራው ሥራ ውጭ በስውር የሚሠራው አንዳች ነገር የለም፡፡ ሥራዎቹን ከሌሎች ሥራዎች ጋር ማጥናትና በንጽጽር መመልከት እውነታውን ለመረዳት በእጅጉ ይጠቅማል፡፡ ከዚህ አልፎ ግን በቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ በግልጽም ሆነ በስውር ሊያደርሱት የፈለጉትን የሃይማኖት ብረዛና ክለሳ ያልተሳካላቸው አጽራረ ቤት ክርስቲያን በሚሰጡት የተሳሳተ መረጃ ተመሥርቶ ትእምርተ ሰላም /የሰላም ምልክት/ የሆነውን ማኅበር መፈረጅ አይገባም፡፡

 

ማኅበረ ቅዱሳን በቤተ ክርስቲያኒቱ መዋቅር ሥር ያለ የቤተ ክርስቲያኒቱን አስትምህሮና መሠረተ እምነት የሚጠብቅ፣ በራሱ አቅምም መሠረት የማስጠበቅ ድርሻውን የሚያበረክት፣ በቅዱስ ሲኖዶስ የጸደቀ ደንብ የተሰጠውና በእርሱም መሠረት ብቻ የሚሠራ ማኅበር እንጂ ራሱን የቻለ የእምነት ሴክትም አይደለም፡፡

 

አባላቱም በአብዛኛው ከፍተኛ ትምህርት የተማሩ፣ በሀገሪቱ ተቋማት ውስጥ ታላቅ ሀገራዊ ሓላፊነትን የሚወጡ፣ ከፊሎቹም በከፍተኛ የሓላፊነት ቦታዎች ላይ ያሉ፣ ለሀገርና ለሕዝብ በሚሰጠው አገልግሎትም ሓላፊነት የሚሰማቸው ዜጎች እንጂ ከክርስትናው አስተምህሮም ሆነ ከኅሊና የተነሣ የማያደርጉትንና ሊያደርጉም የማይችሉትን አክራሪነት ለማኅበሩ አባላት መስጠት አይገባም እንላለን፡፡

 

መንግሥት እንደ ሀገር መሪነቱ የእምነት መሪዎችን ቀርቦ ማወያየቱ፣ ብቅ ጥልቅ፣ ብልጭ ድርግም የሚሉ የእምነት ነክ “ግጭቶች” ለማስወገድ የሚያደርገው ጥረት በሚያስመሰግነውም የችግሩ ሰበዝ ከየት እንደሚመዘዝና የተፈጠረውንም ችግር ከመሠረቱ ለመፍታት ጉዳዩን በጥልቀት ከሚያውቁት ወገኖች መረጃ የመሰብሰቡን ሥራ አጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል፡፡

 

በሀገራችን አሁን ምልክቱ በጉልህ እየታየ ያለው የሃይማኖት አክራሪነት እንቅስቃሴ በብዙኃኑ የክርስትናውም ሆነ የእስልምናው ተከታይ ዘንድ ተቀባይነት የሌለው ተግባር ነው፡፡ የዚሁ አካል የሆነው ማኅበረ ቅዱሳንም እንደ ትናንቱ ሁሉ ዛሬም ጥብዓት በተሞላው ቁርጠኝነት የሚታገለው ነው፡፡ በመሆኑም መንግሥት አሁን እያደረገ ያለው የፀረ አክራሪነት ትግል እንደተጠበቀ ሆኖ በትክክል የአክራሪነት ጠባዩ ከየትኛው አቅጣጫ እንደመጣና ምንጩ የትና ምን እንደሆነ በመለየት ትክክለኛውን ብያኔ ሊሰጥ ይገባል እንላለን፡፡

 

በአንዳንድ አካላት የተሳሳተ አቻ ለመፍጠር ሲባል በጥቅል ለሃይማኖት ተቋማትና ተከታዮቹ የሚቀመጠውም ፍርጃ ሊስተካከል እንደሚገባውና በተገቢው አካል ተገቢውን ሥዕል ማግኘት እንዳለበትም እምነታችን ነው፡፡

 

በመጨረሻም ማኅበረ ቅዱሳን አክራሪነትን እንደሚያወግዝ አበክረን እንገልጻለን፡፡ በተጨማሪም ማኀበሩ ከዚህ በፊት እንዳደረገው ሁሉ ሰላምን አንግቦ ስለ ሰላም ከመንግሥትና መንግሥታዊ ካልሆኑም ሆነ ከሌሎች የሃይማኖት ተቋማት ጋር ለመሥራት ከመቼውም ጊዜ በላይ ዝግጁ መሆኑን ለመገለጽ እንወዳለን፡፡ በዚህም ትልቅ ሀገራዊ ሓላፊነትንና የዜግነት ድርሻውን በመወጣት አመርቂ ውጤት እንደሚያስመዘግብም ያምናል፡፡

 

ወስብሐት ለግእግዚአብሔር


  • ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ 19ኛ ዓመት ቁጥር 23 2004 ዓ.ም.