የመጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር ዓመታዊ ጉባኤውን አካሄደ

ጥቅምት 6 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ

 

የኢትዮጵያ መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር ዓመታዊ ጉባኤውን ቅዳሜ ጥቅምት 3 ቀን 2005 ዓ.ም አዲስ አበባ በሚገኘው ሀርመኒ ሆቴል አካሂዷል፡፡ በጉባኤው ላይ ብፁዕ አቡነ ገብርኤል የቅዱስ ሲኖዶስ አባልና የሲዳማ ጌዲኦ ቡርጂና አማሮ ልዩ ልዩ ወረዳዎች  ሊቀ ጳጳስ እንዲሁም ዶክተር አባ ኀይለ ማርያም መልሴ የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ዲን ጨምሮ ከአብያተ ክርስቲያናት የተወከሉና የማኅበሩ አባላት ተገኝተዋል፡፡

 

የኢትዮጵያ መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር በአሁኑ ጊዜ በትርጉም፣ በኅትመትና በስርጭት ሥራ ላይ ከፍተኛ ትኩረት በመስጠት መጠነ ሰፊ እንቅስቃሴ እያደረገ እንደሚገኝ ያስታወሱት የማኅበሩ ዋና ጸሐፊ አቶ ይልማ ጌታሁን “በዘመናችን እየጨመረ የመጣውን የቅዱሳት መጽሐፍት ፍላጎት ስንመለከት ጥረታችንን ከጊዜ ወደ ጊዜ ማጠናከር እንዳለብን ይታመናል፡፡ ይህንን ተግባር ደግሞ በተገቢው መንገድ ለማከናወን ሁሉም ባለድርሻ አካላት ሓላፊነታቸውን ባግባቡ መወጣት ይኖርባቸዋል” ብለዋል፡፡ ማኅበሩ በያዝነው ዓመት በሰባት ዋና ዋና ዘርፎች ሊሠራቸው ያሰባቸውን ዕቅዶች በሪፖርታቸው ያካተቱት  ዋና ጸሐፊው፥ በአባላት ምዝገባና በቅስቀሳ ዘርፍ ሁሉንም ክርስቲያን ለማሳተፍ መጠነ ሰፊ ቅስቀሳና ምዝገባ ለማከናወን እንዳቀደ አስታውቀዋል፡፡

 

በኢትዮጵያ የመጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር፡- የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ጨምሮ የወንጌላውያን ኅብረትና የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን በአባልነት ተካተዋል፡፡