የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን ተልዕኮ ለማሳካት የገዳማት ድርሻ!!

  • የወርቃማው ዘመን ወርቃማ ደራሲ የአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ የገድል መጽሐፍ  ይመረቃል

 

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ማኅበረ ቅዱሳን ጥንታውያን ገዳማት እና የአብነት ትምህርት ቤቶች ለማጠናከር ላለፉት 10 ዓመታት ዘላቂ የልማት ፕሮጀክቶችን በመቅረጽ ከምዕመናን በተገኘ የገንዘብ ድጋፍ ተግባራዊ ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ በዚህም አበረታች ውጤት ተመዝግቧል፡፡

 

ማኅበሩ ይህንን አገልግሎት አጠናክሮ ለመቀጠል ከ50 ጥንታውያን ገዳማት የተውጣጡ አበምኔቶች በተገኙበት “የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን ተልዕኮ ለማሳካት ገዳማት ያላቸው ድርሻ ”  በሚል መሪ ቃል ቅዳሜ ታኅሣሥ 6 ቀን 2005 ዓ.ም ከቀኑ 7፡00 ሰዓት ጀምሮ በኢትዮጵያ ስብሰባ ማዕከል በተቀናጀ ልማት ለውጥ ማምጣት እንደሚቻል የሚያሳይ መርሐ ግብር ተዘጋጅቷል፡፡

 

እርስዎም በዕለቱ ተገኝተው የመርሐ ግብሩ ተሳታፊ በመሆን የአባቶችን ቡራኬ በመቀበል ድርሻዎትን ይወጡ ዘንድ በአክብሮት ተጋብዘዋል፡፡

ረድኤተ እግዚአብሔር አይለየን

አድራሻ ፡- ስድስት ኪሎ ከምስካየ ኅዙናን መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን ከፍ ብሎ በኢትዮጵያ ስብሰባ ማዕከል
አዘጋጅ ፡-የማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል

dsc03541

የአሰቦት ገዳም የመንገድ ችግር በመቀረፍ ላይ ነው

ኅዳር 20 ቀን 2005 ዓ.ም.
በእንዳለ ደምስስ

•    በሁለት በጎ አድራጊ ወጣቶች የ6 ኪሎ ሜትር የተራራው አስቸጋሪ መንገድ ተሠራ
•    የ12 ኪሎ ሜትሩ መንገድ በመሠራት ላይ ነው

dsc03541የአሰቦት ደብረ ወገግ ቅድሥት ሥላሴና አቡነ ሳሙኤል ገዳም 6 ኪሎ ሜትር የተራራው መውጫ መንገድ በሁለት በጎ አድራጊ ወጣቶች ሙሉ ወጪውን በመሸፈን የጥርጊያ መንገዱን ሥራ ከመስከረም 7 ቀን 2005 ዓ.ም. ጀምሮ  በ17 ቀናት ውስጥ በመሥራት ተጠናቀቀ፡፡

የገዳሙ አበምኔት አባ ተክለ ማርያም ተክለ ፃድቅ ስለ መንገድ ሥራው ሲገልጹ “እግዚአብሔር አነሣሥቷቸው ይህ ቅዱስ ገዳም ያለበትን የመንገድ ችግር ተገንዝበው ሙሉ ወጪውን በመሸፈንና መንገዱ ተሠርቶ እስኪጠናቀቅ ድረስ እዚሁ ከእኛው ጋር በመሆን ሥራውን እየተቆጣጠሩ በአጭር ጊዜ ውስጥ ማጠናቀቅ ተችሏል፡፡ የመንገዱ መሠራት ገዳሙን ከእሳት ቃጠሎ፤ በተለይም የደን ጭፍጨፋ ከሚያካሂዱ አካላትና ከተለያዩ አደጋዎች ይታደገዋል፡፡ ምእመናንም ከዚህ ቅዱስ ሥፍራ በመገኘት በረከት እንዲቀበሉ ያስችላቸዋል፡፡ ለኛ ለገዳማውያንም መውጣት መውረዱን ያቀልልናል፡፡ ሁለቱ ወጣቶች ያከናወኑት በጎ ተግባር ሌሎችም አርአያነታቸውን ሊከተሉ ይገባል  ” ብለዋል፡፡

 

ቴዎድሮስ ሰሎሞን ይባላል፡፡ የ”ዴታና ቢዝነስ ሓላፊነቱ የተወሰነ ግል ማኅበር” ባለቤት ነው፡፡ የ6 ኪሎ ሜትር የተራራውን ጥርጊያ መንገድ ከጓደኛው ጋር በመሆን  ሙሉ ወጪውን በመሸፈን ለመሥራት በቅቷል፡፡ ምን እንዳነሣሣው ጠይቀነው ሲመልስ “አሰቦት ገዳም ላለፉት 10 ዓመታት በዓመታዊ ንግሥ በዓል ላይ በረከት ለማግኘት ተመላልሻለሁ፡፡ ዋነኛ ችግር ነው ብዬ የተመለከትኩትም ምእመናን ተራራውን ለመውጣት የሚያደርጉትን አድካሚ ጉዞ ነበር፡፡ አረጋውያን መውጣት ተስኗቸው በየመንገዱ እያረፉ ሲጨነቁና ሲጠበቡ እመለከታለሁ፡፡ ይህንን መንገድ መች ነው የምሠራው እያልኩ ሳስብ ቆይቻለሁ፡፡ አሰበ ተፈሪ የሚገኙ ወንድሞችን አማክሬያቸው ለኦሮሚያ ግብርና ጉዳዩን በማሳወቅና መንገዱን ለመቀየስ በሚደረገው ጥረት ውስጥ የሚወገዱ ዛፎችን ጉዳይ በመነጋገርና ፈቃድ በመውስድ የጥርጊያ መንገዱን ሥራ ከጓደኛዬ ጋር ተመካክረን የምሠራበትን ዶዘር ቦታው ድረስ በመውሰድ እግዚአብሔር የፈቀደልንን ያህል አባቶች በጸሎት እየተራዱን መንገዱን በማስፋትና በመጥረግ ለመኪናም ሆነ ለሰው በቀላሉ መውጣት እንዲያስችል ተደርጓል፡፡” ብሏል፡፡

“ከዚህ በፊት ወደ ገዳሙ ሄጄ አላውቅም፡፡ ጓደኛዬ  ወደዚህ ገዳም ይመላለስ ስለነበር የገዳሙን ችግር ይነግረኝ ነበር፡፡ አብረን ለመሥራት ተነጋግረን የራሴን ግሬደር በማምጣት በመቀየስና ተለዋጭ መንገድ በማዘጋጀት መንገዱን አስተካክለን ለገዳሙ አስረክበናል፡፡ ከዚህ በረከት ልሳተፍ በመቻሌ ተደስቻለሁ” በማለት የገለጸው ደግሞ የ”ዳክ የኮንስትራክሽን ማሽነሪዎች ኪራይ አገልግሎት” ድርጅት ባለቤት ወጣት ክብሮም ተክሌ ነው፡፡

dsc03547ሥራውን ለመሥራት በገዳሙ በቆዩባቸው ጊዜያት ያስተዋሉትን ሲገልጹም “የገዳማውያኑ ስሜት ልዩ ነው፡፡ የገዳማውያን አባቶችና እናቶች ደስታ ተመልክተናል፡፤ እንኳን እነሱ ለዘመናት የተቸገሩት ቀርቶ እኛም የተሰማን ስሜት መግለጽ ከምንችለው በላይ ነው፡፡ ደስታቸው አስደስቶናል፡፡ ሰዎች ለእግዚአብሔር በሰጡ ቁጥር የሚጎድልባቸው የሚመስላቸው አሉ፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር የተሻለ ነገር እንደሚሰጣቸው ማመን አለባቸው፡፡ ለእግዚአብሔር መስጠት አያጎድልም ይጨምራል እንጂ፡፡ የእኛን ደስታ ሌሎችም እንዲጋሩት እንፈልጋለን፡፡ ያደረግነው ነገር ትንሽ ቢሆንም ከእግዚአብሔር ጋር ከሆንክ ትረካለህ፡፡ ወደፊትም አቅማችን እያዳበርን ሌሎች ገዳማትን የመርዳት እቅድ አለን፡፡” በማለት ሁለቱ በጎ አድራጊ ወጣቶች ተናግረዋል፡፡

ማኅበረ መነኮሳቱ ስለተከናወነው የመንገድ ሥራ  ሲገልጹ “ብርሃን አየን፡፡ ለዘመናት የተቸገርንበትና ከአቅማችን በላይ የሆነውን ነገር እግዚአብሔር ደብቆ ያስቀመጣቸው ልጆቹን በመላክ አስወገደልን” ብለዋል፡፡

በተያያዘ ዜና ከአሰቦት ከተማ መገንጠያ እስከ ተራራው መውጫ ሥር ድረስ 12 ኪሎ ሜትር የሚፈጅ ሲሆን ገዳሙ ያለበትን የመንገድ ችግር ለመቅረፍ ከሚመለከተው ከክልሉ መንገዶች ባለስልጣን መሥሪያ ቤት ጋር  በመወያየት እንዲሁም አዲስ አበባ ከሚገኙ ምእመናን ጋር በመነጋገር  የመንገድ ሥራውን የሚቆጣጠርና የሚመራ አንድ ኮሚቴ አዋቅሮ በመንቀሳቀስ ላይ ይገኛል፡፡ በዚህም መሠረት በፌደራል መንገዶች ባለሥልጣን ሁሉን አቀፍ ተደራሽነት ያለው የገጠር መንገድ ፕሮግራም (Universal Rural Road Access Program) – URRAP መንገዱን ለመሥራት ባጠናው ጥናት መሠረት እሰከ 6 ሚሊዮን ብር እንደሚፈጅና 1 ሚሊዮን ብር ገዳሙ ከቻለ ቀሪውን ወጪ በመንግሥት እንደሚሸፈን በመግለጹ ስምምነት ላይ በመድረስ ሥራው ሊጀመር ችሏል፡፡

 

“ገዳሙም ባቋቋመው ኮሚቴ መሠረት ገንዘብ ከምእመናን በማሰባሰብ ላይ የሚገኝ ሲሆን የመንገዱ ሥራም የመጀመሪያውን ዙር በማጠናቀቅ ወደ ሁለተኛው ክፍል ተሸጋግሯል፡፡ ሥራውንም በቅርበት በመከታተል ላይ እንገኛለን፡፡ ገዳሙ ገንዘብ ለማሰባበሰብ ከፍተኛ ጥረት በማድረግ ላይ ሲሆን ከምእመናን  የታቀደውን ያህል ለማሰባበሰብ ባይቻልም በተገባው ቃል መሠረት የመጀመሪያ ዙር ክፍያ ተፈጽሟል፡፡ ቀጣዩንም ሥራ ለማከናወን የገንዘብ ማሰባሰቡ ይቀጥላል“ በማለት የኮሚቴው የቴክኒክ ክፍል ሓላፊ የሆኑት ኢንጂነር ዮሐንስ ዘውዴ  ገልጸዋል፡፡

 

በተጨማሪም ማኅበረ ቅዱሳን ገዳሙ ያለበትን የውኃ ችግር ለመቅረፍ በቅርቡ የባለሙያዎች ቡድን በመላክ አጥንቶ መመለሱን ከቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡

 

በ13ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የተገደመው የአሰቦት ደብረ ወገግ ቅድሥት ሥላሴና አቡነ ሳሙኤል ገዳም በተደጋጋሚ የእሳት ቃጠሎ ያጋጠመው ሲሆን እሳቱን ለመጥፋት በተደረገው ጥረት ውስጥ የተራራው አስቸጋሪነት ትልቁ ፈተና እንደነበር ይታወሳል፡፡

ledet04

የድንግሊቱም ስም ማርያም ነበር

ኅዳር 19 ቀን 2005 ዓ.ም.

በመ/ር ሰሎሞን መኩሪያ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ

ledet04በቤተ እስራኤል ስም ጠባይን፣ ግብርን፣ ሁኔታን እንደሚገልጥ ሁኖ ይሰየማል፡፡ ስለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም “ማርያም” የሚለውን ስያሜ ከማየታችን በፊት ስለ ድንግል ማርያም አባቶቻችን በነገረ ማርያም ያሉትን ጥቂት እንመለከታለን፡፡ “ነቢዩ ኢሳይያስ በትንቢቱ በም.1፥9 ላይ እንደተናገረ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር ዘርን ባያስቀርልን ኖሮ እንደ ሰዶም በሆንን ገሞራንም በመሰልን ነበር፡፡” እንዳለ በኦ.ዘፍ.ም.19፥1 ጀምሮ እንደተጻፈ የሰዶምና የገሞራ ሰዎች በበደላቸው ምክንያት እንደተደመሰሱ /እንደጠፉ/ እናነባለን፡፡ አዳምና ልጆቹ በሲዖል ባህር ሰጥመን እንዳንቀር እግዚአብሔር በቸርነቱ ንጽህት የሆነች ዘር መርገመ ሥጋ መርገመ ነፍስ የሌለባት በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስ እያማለደች የምታሰጥ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ባያስቀርልን ከእርሷም መርገመ ሥጋ መርገመ ነፍስን የሚያርቅ በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስ የሚያድል የባሕርይ አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ ተወልዶ በሞቱ ሞታችንን ባይደመስስ ወደ ሕይወት ባይመልሰን ኖሮ መኖሪያችን ሲዖል ነበር፡፡

 

ለፍጥረት ሁሉ መዳን ምክንያት ያደረጋት ንጽሕት ዘር እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ትውልዷ በአባቷ በኩል ከንጉሡ ከዳዊት ወገን ነው፡፡ በእናቷ በኩል ከሊቀ ካህናቱ ከአሮን ወገን ነው፡፡ የአባቷ ስም ቅዱስ ኢያቄም የእናቷ ስም ቅድስት ሐና  ይባላል፡፡ ሁለቱም በሕግ በሆነ ቅዱስ ጋብቻ ሲኖሩ ለብዙ ዘመን ልጅ አልነበራቸውም፡፡ ልጅ ይሰጠናል በማለት ተስፋ እግዚአብሔርን በጾም በጸሎት ደጅ እየጸኑ ኖሩ እንጂ፡፡ በዘመኑ ልጅ ያልወለደ ኀጢአተኛ፣ እግዚአብሔር የተጣላው ተደርጎ ይወሰድ ስለነበረ ወደ ቤተ እግዚአብሔር የሚያመጡትን መብዓ አይቀበሏቸውም፤ ይሰድቧቸው፣ ያሽሟጥጧቸውም ነበር፡፡ ይህንን ሁሉ ታግሰው ሲኖሩ እግዚአብሔር ትእግሥታቸውን ተመልክቶ የሚወልዷትን የድንግል ማርያምን ነገር በህልም ገለጸላቸው የእግዚአብሔርን ፈቃድ ሲጠብቁ እመቤታችን ነሐሴ 7 ቀን ተፀንሳለች፡፡ በተፀነሰች ጊዜ ብዙ ተአምራት ተደርጓል፡፡ የሃናን ማሕፀን እየዳሰሱ፡- ብዙ እውራን አይተዋል፣ ድውያን ተፈውሰዋል፣ ምውታን ተነሥተዋል፡፡ ይህንን የተመለከቱ አይሁድ ቅዱስ ኢያቄምን እና ቅድስት ሐናን በድንጋይ ወግረው በእሳት አቃጥለው ሊገድሏቸው በጠላትነት ሲነሡ የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ሊባኖስ ወደ ሚባል ተራራ ይዟቸው ወጣ፡፡ በዚያ ሳሉ በግንቦት 1 ቀን ከፀሐይ 7 እጅ የምታበራ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተወለደች፡፡ ጠቢቡ ሰሎሞን በመኀልይ በም.4፥8 ላይ እንደተናገረ “ሙሽራዬ ሆይ ከሊባኖስ ነይ…. ከአንበሶች ጉድጓድ ከነብሮችም ተራራ ተመልከች፡፡” እንዳለ ይህ ትንቢት ተፈጸመ በተወለደች በ8ኛው ቀን ስሟን “ማርያም” ብለው አወጡላት ለመሆኑ ማርያም ማለት ምን ማለት ነው?

 

ሀ. ማርያም ማለት ጸጋ ወሀብት ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ዳዊት በመዝ.126፥3 ላይ ልጆች የእግዚአብሔር ስጦታ ናቸው፡፡” ብሎ እንደተናገረ አባቷ ቅዱስ ኢያቄም እናቷ ቅድስት ሐና ከእግዚአብሔር የተሰጠችን ስጦታችን፣ ሀብታችን ናት ብለው “ማርያም” አሏት፡፡ ለጊዜው ለእናት እና ለአባቷ ስጦታ ሁና ትሰጥ እንጂ ለፍፃሜው ለፍጥረት ሁሉ እናት አማላጅ ሆና ከእግዚአብሔር የተሰጠች ናት በተለይ ለክርስቲያኖች በእምነት እናትነቷን እና አማላጅነቷን ለሚቀበሉ በዮሐንስ ወንጌላዊ አማካኝነት እናት ሁና የተሰጠች ልዩ ስጦታ ናት አምላካችን ክርስቶስ በቀራኒዮ አደባባይ በመስቀል ተሰቅሎ ቅዱስ ሥጋውን ቆርሶ ክቡር ደሙን አፍስሶ ለድኅነታችን እንደሰጠን ሁሉ እናቱንም እናት ትሁናችሁ ብሎ ሰጥቶናል፡፡” ዮሐንስ ወንጌላዊ ወደ ቤቱ እንደወሰዳት እኛም ወደ ቤተ ልቦናችን ልናስገባት ጣዕሟን በአንደበታችን ፍቅሯን በልቦናችን ልናሳድረው ያስፈልጋል፡፡ ዮሐ.19፥26 የድንግል ማርያም ጣዕሟ በአንደበታችን ፍቅሯ በልቦናችን ይደር፡፡ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤልም ከእግዚአብሔር ተልኮ ወደ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም መጥቶ እያመሰገናት እየተሳለማት የነገራት ነገር ቢኖር እርሷ “ምልዕተ ጸጋ ወክብር” እንደሆነች ነው፡፡ ሉቃ.1፥28 እንግዲህ መልአኩ ከእግዚአብሔር አግኝቶ የእመቤታችንን ነገር እንደነገረን የጐደለባት ጸጋ የሌለ እመቤት ናት እና እኛ ደግሞ ብዙ ነገር ጐድሎብናልና ከተትረፈረፈ ጸጋዋ እንድታድለን ምልዕተ ጸጋ ምልዕተ ውዳሴ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ልንማፀናት ይገባል፡፡ እመቤታችን ጸጋ በረከት ታድለን፡፡

 

ለ. ማርያም ማለት ፍፅምት ማለት ነው፡ “ፍፅምት” ማለት እንከንና ጉድለት የሌለባት ማለት ነው፡፡ እመቤታችን ለጊዜው መልክ ከደምግባት ጋር አስተባብራ በመገኘቷ ፍፅምት ተብላለች፡፡ እግዚአብሔር አምላክ በባሕርይው ቅዱስ ነው፡፡ ዘሌ.19፥2 ቅዱስ እና ንፁሐ ባሕርይ የሆነ እግዚአብሔር ዓለምን ለማዳን በወደደ ጊዜ አባ ሕርያቆስ በቅዳሴው እንደተናገረ “እግዚአብሔር በሰማይ ሁኖ ምሥራቁን እና ምዕራቡን ሰሜኑን እና ደቡቡን ዳርቻዎችን ሁሉ ተመለከተ እንዳንቺ ያለ አላገኝም የአንቺን መዓዛ ወደደ፤ ደምግባትሽን ወደደ፤ የሚወደውን ልጁን ወደ አንቺ ሰደደ” እንዲል፡፡ ንፁሐ ባሕርይ እግዚአብሔር ለማደሪያነት /ለተዋሕዶ/ እመቤታችንን መረጠ እርሷም ፍፅምት ናት የአዳም መርገም ያልወደቀባት /ጥንተ አብሶ/ የሌለባት ጠቢቡ ሰሎሞን በመኀል.4፥7 ላይ እንደተናገረ እንዲህ ብሎ “ወዳጄ ሆይ ሁለንተናሽ ውብ ነው ነውር የለብሽም፡፡” እንዲል እንኳን የአምላክ እናት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቀርቶ ወዳጆቹ ቅዱሳን እንኳን አካሄዳቸውን ከእግዚአብሔር ጋር ሲያደርጉ ከፍፁምነት ማዕረግ ይደርሳሉ ይህንንም ቅዱስ መጽሐፍ ይመሰክርላቸዋል፡፡ ለምሳሌ ኖኅ በትውልዱ ጻድቅ ፍፁምም ሰው ነበር  ዘፍ.6፥9፡፡ ኢዮብም ፍጹምና ቅን እግዚአበሔርንም የሚፈራ ከክፋትም የራቀ ነበር ኢዮብ 1፥1፡፡ ይላል፡፡ የኖኅን እና የኢዮብን አምላክ የወለደች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ፍፅምትነቷ አያጠራጥርም፡፡ የድንግል ማርያም ጸጋ በረክት ይደርብን፡፡

 

ሐ. ማርያም ማለት የሕያዋን እናት ማለት ነው፡፡ ዘፍ.3፥20 ላይ “አዳምም ለሚስቱ ሔዋን” ብሎ ስም አወጣ የሕያዋን ሁሉ እናት ናትና፡፡ ይላል በእርግጥ ሔዋን ለሕያዋን ሁሉ ማለትም ለፍጥረት ሁሉ እናት ናት ግን ፍጥረትን ሁሉ አስጐድታለች ማለትም አትብሉ ተብሎ ከእግዚአብሔር የታዘዘውን ዕፀ በለስን በልታ ለባሏ ለአዳም በማብላቷ በሰው ልጆች ላይ የሞት ሞት እንዲመጣ /እንዲፈርድባቸው/ ምክንያት ሁናለች ከእርሷ ምክንያተ ስህተትነት የተነሣ የገነት ደጃፎች ተዘጉ በምትገለባበጥ የኪሩብ ሰይፍ እንድትጠበቅ ሆነ፡፡ ዘፍ.3፥24 በዚህ የተነሣ በሰው ልጆች ላይ 5500 ዘመን ሞት ሰለጠነ፡፡ አዳም ግን “ሔዋንን” የሕያዎን ሁሉ እናት ብሎ በትንቢት የተናገረላት ሔዋንን ሳይሆን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ነው፡፡ ሊቁ ቅዱስ ኤፍሬም በውዳሴ ማርያም ዘሐሙስ “በእንተ ሔዋን ተዐፅወ ኆኅተ ገነት ወበእንተ ማርያም ድንግል ተርኀወ ለነ” ይላል ትርጉሙም “ስለ ሔዋን የገነት ደጅ ተዘጋ ዳግመኛ ስለ ድንግል ማርያም ተከፈተልን” ማለት ነው፡፡ ሔዋን ሕያዋንን ሁሉ አስጐዳች ዳግማዊት ሔዋን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ደግሞ ለሕያዋን ሁሉ እናት ሆና ፍጥረቱን ሁሉ ለማዳን ምክንያት ሆነች፡፡

 

ሕያዋን የሚባሉት ጥምቀተ ክርስትና ያላቸውን ወልድ ዋሕድ ብለው በልጇ በኢየሱስ ክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት የሚያምኑትን ክርስቲያኖችን ነው፡፡ እነዚህ ሕያዋን  ናቸው፡፡ ጌታ በቅዱስ ወንጌሉ “በወልድ ያመነ የዘለዓለም ሕይወት አለው ያላመነ ግን አሁን ተፈርዶበታል፡፡” እንዲል ዮሐ.3፥37 ደግሞም ሰው ሰው ተብሎ በሕይወት ለመኖር ከእናት ከአባቱ መወለድ ግድ እንዲሆንበት ክርስቲያንም ክርስቲያን ይባል ዘንድ ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ በጥምቀት መወለድ አለበት ዮሐ.3፥5፡፡ የእነዚህ እናታቸው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ናት፡፡ አንድም ሕያዋን የሚላቸው ለገነት ለመንግሥተ ሰማያት የሚያበቃቸውን የነፍስ ሥራ ሠርተው በጽድቅ የተሸለሙ ቅዱሳን ጻድቃን ሰማዕታት ናቸው የእነዚህ እናታቸው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ናትና ስማን “ማርያም” አሉት፡፡

 

መ. ማርያም ማለት ከፍጡራን ሁሉ በላይ ከፈጣሪ በታች የከበረች ደግ ፍጥረት ማለት ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላክ የሚታየውንና የማይታየውን ብዙ ፍጥረት ፈጥሯል ከእነዚህ ፍጥረታት መካከል ግን ሰው እና መላእክት ክብሩን እንዲወርሱ ስሙን እንዲቀድሱ ለይቶ ፈጥሮአቸዋል፡፡ ከሰው መላእክት በቅድስና ለእግዚአብሔር የቀረቡ ናቸው፡፡ ከእነዚህ መላእክት መካከል ስድስት ክንፍ ያላቸው ብዙ ዐይኖች ያሏቸው የእግዚአብሔርን ዙፋን የሚሸከሙ እግዚአብሔርም በዘፈቀደ ለወዳጆቹ ሲገለጽ የሚታይባቸው ክብር ያላቸው ናቸው፡፡ በፈጣሪያቸው ፊት ግን ሲታዩ ትእምርተ ፍርሐት አላቸው ከዙፋኑ የሚወጣው እሳት እንዳያቃጥላቸው በሁለት ክንፋቸው ፊታቸውን ይሸፍናሉ፤ ገጽህን ማየት አይቻለንም ሲሉ፤ በሁለት ክንፋቸው ከዳርቻ እስከ ዓለም ዳርቻ ይወጣሉ ይወርዳሉ ባህርይህን ተመራምሮ መድረስ አይቻልም ሲሉ፡፡ እንዲህ ባለ ፍርሐት ፈጣሪያቸውን “ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ እግዚአብሔር ጸባዖት ፍጹም ምሉዕ ሰማያተ ወምድረ ቅድሳተ ስብሐቲከ” እያሉ ያመሰግናሉ፡፡ ራዕ.4፣ ኢሳ.6 እነዚህ ከፍጡራን ሁሉ የከበሩ ለእግዚአብሔርም የቀረቡ ናቸው ከእነዚህ ግን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ትበልጣለች፡፡ ምክንያቱም እነርሱ እንዲህ ከሚንቀጠቀጡለት ከሦስቱ ቅዱስ አንዱን ቅዱስ ወልደ እግዚአብሔርን ዘጠኝ ወር ከ5 ቀን በማሕፀኗ የተሸከመች አዝላ የተሰደደች በማስተማር ዘመኑ ያልተለየች እስከ እግረ መስቀል ድረስ የነበረች የአምላክ እናት ናትና ስለዚህም ቅዱስ ኤፍሬም ሲናገር “ይእቲ ተዓቢ እም ኪሩቤል ወትፈደፍድ እም ሱራፌል እስመ ኮነት ታቦተ ለአሐዱ ዘእም ቅድስት ሥላሴ” ብሏል በእውነትም ከኪሩቤል እና ከሱራፌል ትበልጣለች ከቅድስት ሥላሴ አንዱን ወልደ እግዚአብሔርን በሕቱም ድንግልና ፀንሳ በሕቱም ድንግልና ወልዳዋለችና ይህ ጸጋ ለእመቤታችን እንጂ ከፍጡራን መካከል ለሌላ ለማንም አልተሰጠምና ከነገደ መላእክት ከደቂቀ አዳም በክብር የሚመስላት በጸጋ የሚተካከላት የለም፤ ከፍጡራን በላይ ያሰኛታል፡፡ “ከሴቶች ተለይተሽ የተባረክሽ ነሽ….. ካንቺ የሚወለደው ቅዱስ ነው፡፡ የልዑል እግዚአብሔርም ልጅ ይባላል፡፡” ሉቃ.1፥28፣ ሉቃ.1፥35 እንዲል፡፡

 

ሠ. ማርያም ማለት መርሕ ለመንግሥተ ሰማያት ማለት ነው /መንግሥተ ሰማያት መርታ የምታስገባ/ ማለት ነው፡፡ የቀደመው ፍጥረት የታደሰባት ወደ ቀደመ ርስቱ ወደ መንግሥተ ሰማያት ለመግባት ምክንያተ ድሂን የሆነችው እመቤታችን ድንግል ማርያም ናት ዛሬም ያለው ፍጥረት ወደ መንግሥተ ሰማያት ለመግባት የድንግል ማርያም ምልጃ ያስፈልገዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያን የእመቤታችንን መርቶ መንግሥተ ሰማያት የምታስገባ የመሆኗን ነገር በምሳሌ እንዲህ ስትል ታስተምራለች፡፡ በዘፀ.ም.32 እና 34 ላይ ተጽፎ እንደምናገኘው ሙሴ በደብረ ሲና 40 መዓልት 40 ሌሊት ከጾመ ከጸለየ በኋላ እግዚአብሔር ተቀብሎ ከተራራው ሲወርድ እስራኤል ጣዖት አቁመው ሲሰግዱ ተመለከተ በዚህ ጊዜ ፍቅረ እግዚአብሔር ቢያቃጥለው በፅላቱ ጣዖቱን መታው ፅላቱ ተሰበረ ጣዖቱ ደቀቀ፡፡ ወደ እግዚአብሔር ሲያመለክት ከማይነቅዝ እንጨት ሠርቶ ወደ ተራራው እንዲወጣ በዚያም እንደ ቀድሞው እንዲጾም እንዲጸልይ እግዚአብሔር አዘዘው እርሱም እንደታዘዘው አደረገ እግዚአብሔርም በተሰወረች ጣት ትዕዛዛቱን ጻፈበት ለሙሴም ሰጠው ሙሴም ይህንን ይዞ ከተራራው ሲወርድ ብርሃን ተሳለበት እስራኤል በዚች ፅላት እየተመሩ የዮርዳኖስን ባህር ከፈሉ ኢያሱ.3፥14-17 የኢያሪኮን ቅፅር ናዱ /አፈረሱ/ ኢያ.6፥8 ምድረ ርስት ከነዓን ገብተው ርስት ተካፈሉ፡፡ በዚህ ምሳሌ የቀደመው ከእግዚአብሔር ዘንድ ለሙሴ የተሰጠው የእንቁ ፅላት የአዳም የፅላቱ መገኛ ከእግዚአብሔር እንደሆነ ሁሉ ለአዳምም እናትና አባት መገኛ የሚሆን የለውም ወድቆ መሰበሩ ሕግ ትዕዛዝ በመተላለፉ ከፈጣሪው መለየቱን ያመለክታል፡፡ ፅላቱ እንደተሰበረ ይቅር እንዳላለ አዳምም እንደወጣ ይቅር አላለም በንስሓው ተቀብሎታልና፡፡ ሁለተኛይቱ ፅላት እመቤታችን ሙሴ ሠርቶ መውሰዱ እመቤታችን በዘር መገኘቷን ከቅድስት ሐና ከቅዱስ ኢያቄም መወለዷን ያመለክታል፡፡ ከማይነቅዝ እንጨት መሥራቱ እመቤታችን በሐልዮ /በማሰብ/ በነቢብ /በመናገር/ በገቢር /መሥራት/ ኀጢአት እንዳልፈጸመች ንፅናናዋን ቅድስናዋን ያመለክታል፡፡ በፅላቱ ላይ በእግዚአብሔር ጣት የተጻፈ የእግዚአብሔር ቃል ነው፡፡ በማሕፀነ ድንግል የተቀረጸው የአብ አካላዊ ቃል ኢየሱስ ክርስቶስ እንደሆነ ያመለክታል፡፡ ዮሐ.1፥1 “በመጀመሪያ ቃል ነበረ ቃልም እግዚአብሔር ነው” ዮሐ.1፥14 የቃል ሥጋ ሆነ በእኛም አደረ” እንዳለ፡፡ በዚያች ፅላት እስራኤል ባህር እንደተከፈለላቸው፣ ቅፅር እንደተናደላቸው ተመርተው ርስት እንዲወርሱ ጥንተ ጠላታትን ዲያብሎስ ተሸንፎ በእመቤታችን በተሰጣት ቃል ኪዳን አማላጅነት ከገቡ መውጣት ካገኙ ማጣት የሌለባት መንግሥተ ሰማያትን ለመውረስ እድል አገኘን፡፡ ከብዙ በጥቂቱ ከላይ የተጠቀሰውን አልን እንጂ ስለ እመቤታችንስ የተነገረው ብዙ ነው፡፡ የድንግል ማርያም ጣዕሟ በአንደበታችን ፍቅሯ በልቡናችን ይደርብን በአማላጅነቷ ለርሥተ መንግሥተ ሰማያት ታብቃን አሜን፡፡

dn. reda wube

ዲያቆን ረዳ ውቤ አረፉ

ኅዳር 17 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ


dn. reda wubeበሲዳሞ  ክፍለ ሀገር፣ ቡሌ ወረዳ በሚገኘው ጎንፈራ ቀበሌ፥ ከወላጅ አባታቸው አቶ ውቤ አብዲና ከእናታቸው ከወ/ሮ መሰለች ተመስገን፥ መጋቢት 5 ቀን 1955 ዓ.ም የተወለዱት ዲ/ን ረዳ ውቤ፤ ባደረባቸው ሕመም ምክንያት በልዩ ልዩ የሕክምና መስጫ ተቋማት ሲረዱ ቆይተው  በ50 ዓመታቸው ኅዳር 10 ቀን 2005 ዓ.ም ከዚህ ዓለም በሞተ ሥጋ ተለይተው፥ ኅዳር 11 ቀን 2005 ዓ.ም በቡራዩ ፄዴንያ ስመኝ ማርያም ገዳም ሥርዓተ ቀብራቸው ተፈጽሟል፡፡

 

ዲያቆን ረዳ ውቤ ከልጅነት ዕድሜያቸው አንሥቶ ለቤተ ክርስቲያን  ትምህርትና አገልግሎት ከነበራቸው ጽኑ ፍቅር የተነሣ፥ ከመምህራቸው አባ ኀይለ ማርያም ግብረ ዲቁናን ተምረው በ1969 ዓ.ም በወቅቱ የሲዳሞ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ከነበሩት ብፁዕ አቡነ በርቶሎሚዎስ መዓረገ ዲቁናን ተቀብለዋል፡፡ከዚህ በኋላ ከ1969 እስከ 1977 ዓ.ም የይርጋለም ደብረ መዊዕ ቅዱስ ሚካኤል ሰንበት ትምህርት ቤትን በመመሥረትና ለአምስት ዓመታት በሰብሳቢነት፣ እንዲሁም ሰንበት ትምህርት ቤቱን በመወከል በደብሩ የሰበካ ጉባኤ በጸሓፊነት አገልግለዋል፡፡ ዲያቆን ረዳ ከ1978 እስከ 1980 ዓ.ም በባሕር ዳር ፖሊ ቴክኒክ ኢንስቲቲዩት በነበራቸው የትምህርት ቆይታ፥ በባሕር ዳር ፈለገ ገነት ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ትምህርት ቤት በአባልነት ተመዝግበው የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች  ወደ ቤተ ክርስቲያን እንዲሄዱና በሰንበት ትምህርት ቤት እንዲሳተፉ፡ አልፎም ዛሬ በመላ ሀገሪቱ እየተካሄደ ላለው የግቢ ጉባኤ መጀመር ምክንያት ለመሆን የበቁ ሰው ናቸው፡፡

 

በዲ/ን ረዳ ውቤ ሕይወትና በአገልግሎታቸው ዙሪያ ከተዘጋጀው የግለ ሕይወት ታሪካቸው ለመረዳት እንደተቻለው፡- የመጀመሪያዎቹን ክርስቲያኖች የአንድነት ኑሮን መሠረት በማድረግ በተቋቋመው የጽርሐ ጽዮን ዘተዋሕዶ አንድነት ኑሮ ማኅበርን ከጥቅምት 2 ቀን 1990 ዓ.ም ጀምሮ በመቀላቀል ነፍሳቸው ከሥጋቸው እስክትለይ በዚያው ቦታ ቆይተዋል፡፡ በዚሁ ቆይታቸውም ማኅበሩን በልዩ ልዩ ሓላፊነቶች ያገለገሉ ሲሆን ማኅበሩ ባካሄዳቸው 15 ዙር የሰባክያነ ወንጌል ሥልጠናዎች ላይ በመምህርነት ተሳታፊ ሆነዋል፡፡ በተጨማሪም ከ1990 ዓ.ም. ጀምሮ እስከ ዕለተ ረፍታቸው የማኅበሩ የሰባክያነ ወንጌል ማሠልጠኛ ትምህርት ክፍል ሓላፊ በመሆን አገልግለዋል፡፡

 

መላ ዘመናቸውን ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የሰጡት ዲያቆን ረዳ ውቤ  የሳንባ፣ የልብና የጨጓራ ሕመማቸውን ታግሰው ቤተሰባቸውና ማኅበሩ እንዳይጨነቅ ሕመምተኛ ሳይመስሉ የተጣለባቸውን ሓላፊነት በትጋት ተወጥተዋል፡፡ዲያቆን ረዳ ባለትዳርና የአራት ልጆች አባት ነበሩ፡፡

abune petros statute

የብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ሐውልት ለጊዜው ከቦታው ይነሣል

ኅዳር 15 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

የአዲስ አበባ ከተማ ትራንስፖርት ችግርን ለመቅረፍ እንዲያስችል በሚዘረጋው የቀላል ባቡር መሥመር ዝርጋታ ምክንያት የብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ሐውልት እንደሚነሣ የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን አስታወቀ፡፡

abune petros statute

አቶ አበበ ምሕረቱ የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን የኮምኒኬሽን አገልግሎት ክፍል ሓላፊ የሐውልቱ መነሣት ያስፈለገበት ዋነኛ ምክንያት ምን እንደሆነ ሲገልጹ “በቀላል ባቡር መስመር ዝርጋታ ምክንያት መንገዱ ከዳግማዊ አፄ ምኒልክ አደባባይ ጀምሮ ወደ አውቶቡስ ተራ የሚወስደው መንገድ አትክልት ተራ ድረስ ባቡሩ በዋሻ ውስጥ ነው የሚያልፈው፡፡ በተጨማሪም የባቡሩ መስመር  ከምኒልክ አደባባይ ወደ ሽሮ ሜዳ ይዘረጋል፡፡ እንደሁም ከአውቶቡስ ተራ ወደ ቅድስት ልደታ ለማርያም የሚታጠፈው መስመር መነሻም ነው፡፡ ስለዚህ በአሁኑ ወቅት ከማዘጋጃ ቤት አጥር ጀምሮ ወደ ትግበራ የተገባበት ሁኔታ ላይ እንገኛለን፡፡ ሥራው ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ሀውልት ሲደርስ ስዊድን አገር የሚገኘውና ከፍተኛ ልምድ ያለው ዓለም አቀፍ አማካሪ ድርጅት ሥራውን በበላይነት የሚቆጣጠረው ሲሆን በሚያስመጣቸው ባለሙያዎች አማካይነት በክብርና በጥንቃቄ ሐውልቱን አንሥቶ የዋሻው ግንባታ እንደተጠናቀቀ አንዲትም ሣ/ሜትር ሳይዛነፍ እንደነበረ በቦታው ላይ በክብር እንዲያስቀምጥ ይደረጋል፡፡ ሐውልቱ የሀገር ቅርስና ሀብት ነው፤ ለዚህም ከፍተኛ ጥንቃቄ የተሞላበት ሥራ ይሠራል፡፡” ብለዋል፡፡

 

ፕሮጀክቱ የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን ብቻውን የሚያከናውነው ሳይሆን የአዲስ አበባ የጽዳትና ውበት ኤጀንሲ፤ የአዲስ አበባ ቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለስልጣን፤ ባሕልና ቱሪዝም ቢሮዎች፤ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር እንዲሁም የሃይማኖት አባቶች ጋር በመሆን እንደሚከናወን የገለጹት የኮርፖሬሽኑ የኮምኒኬሽን አገልግሎት ክፍል ሓላፊው  በጉዳዩ ላይ ሰፊ ውይይት በማድረግ ወደ ትግበራ እንደተገባ አጽንኦት ሰጥተው ተናግረዋል፡፡

 

“ሐውልቱ ተነሥቶ የት ነው የሚቆየው?” በማለት ላቀረብንላቸው ጥያቄ ምላሽ ሲሰጡም “ሐውልቱ በክብር ከተነሣ በኋላ ባለሙያዎቹ በሚያቀርቡት ጥናት መሠረት ባለ ድርሻ አካላት ተወያይተው በሚዘጋጀው አስተማማኝና ምቹ ሥፍራ ላይ እንዲቀመጥ ይደረጋል፡፡ በመጨረሻም በክብር ወደ ቦታው ይመለሳል” ብለዋል ፡፡

 

የዳግማዊ አፄ ምኒልክ ሐውልት በተመለከተም ”አሁን ባለው ዲዛይን መሠረት ሐውልቱን ስለማይነካው አይነሣም” በማለት ምላሻቸውን ሰጥተዋል፡፡

 

“ይህንን ጉዳይ ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አሳውቃችኋል?” ብለናቸውም “ፕሮጀክቱ የሁላችንም ነው፡፡ የሀገር ነው፡፡ ጉዳዩ ይመለከታቸዋል ለተባሉት አካላት ሁሉ አሳውቀናል፡፡” በማለት የመለሱ ሲሆን ወደፊትም ተቀራርበው እንደሚሠሩ ገልጸዋል፡፡

 

“ሌላ ዲዛይን ለመሥራት ለምን አልተሞከረም?” ላልናቸው ሲመልሱም “ዲዛይኑ ማእከላዊውን መንገድ ይዞ ነው የተሠራው፡፡ ይህንኑ ተከትሎ ይከናወናል፡፡”በማለት መልሰዋል፡፡

 

በመጨረሻም “ሐውልቱ ከተነሣ በኋላ ወደ ቦታው ለመመለሱ ሓላፊነቱን ማነው የሚወስደው?” ብለን ለጠየቅናቸው  “መንግሥት የህዝብን ችግር ለመፍታት በሚያደርገው ጥረት ውስጥ ሁሉም ሀላፊነቱን ወስዶ የሚሰራ ይሆናል፡፡ ባለ ድርሻ አካላቱም የመንግሥትን ሥራ የሚያስፈጽሙ በመሆናቸው ሓላፊነት አለባቸው፡፡ ስለዚህ ሁሉም ሓላፊነት አለበት” ብለዋል፡፡

የማኅበሩ የቴሌቪዥን ፕሮግራም ተራዘመ

ኅዳር 11 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

የማኅበረ ቅዱሳን የኅትመትና ኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ዋና ክፍል በኢቢኤስ የቴሌቪዥን መርሐ ግብር ለመጀመር ከፍተኛ ጥረት እያደረገ እንደሚገኝ ይታወቃል፡፡ ነገር ግን በእኛ በኩል ዝግጅታችንን ለመጀመር ዝግጁ ሆነን እየተጠባበቅን የምንገኝ ሲሆን ከኢቢ ኤስ ቴሌቪዥን  በኢትዮጵያና በመካከለኛው ምሥራቅ አገራት የጀመረው ስርጭት ከኅዳር 5 ቀን 2005 ዓ.ም. ጀምሮ ካልታወቀ አቅጣጫ በተደረገ ከፍተኛ የሳተላይት ሲግናል ማዛባትና እቀባ ወይም “ጃሚንግ” እክል እንደደረሰበት አስታውቋል፡፡ በመሆኑም ስርጭቱ እንደተስተካከለ የማኅበረ ቅዱሳን ቴሌቪዥን መርሐ ግብር የሚቀጥል ሲሆን በትእግሥት እንድትጠባበቁን በአክብሮት እንጠይቃለን፡፡

ማእከላቱ ጠቅላላ ጉባኤያቸውን አካሄዱ

ኅዳር 11 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን  ማኅበረ ቅዱሳን  የአሰላ፣ የአምቦ፣ የፍቼ፣ የደብረ ብርሃን፣ የወሊሶ እንዲሁም የወልቂጤ ማእከላት ከጥቅምት 25  እስከ ኅዳር 2 ቀን 2005 ዓ.ም ባሉት ጊዜያት ጠቅላላ ጉባኤያቸውን ከወረዳ ማእከላት፣ ከግንኙነት ጣቢያዎች፣ ከግቢ ጉባኤያት የተወከሉ አባላት፣ የየሀገረ ስብከቱ ተወካዮች፣ የወረዳ ሊቃነ ካህናት፣ የአድባራት አስተዳዳሪዎች፣ የሰንበት ትምህርት ቤት ተወካዮች እና  የማኅበረ ቅዱሳን የዋናው ማእከልና የመሐል ማእከላት ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት ልዑካን በተገኙበት አካሂደዋል፡፡

 

ለጉባኤያቱ በወጣው  መርሐ ግብር መሠረት በ2004 ዓ.ም  ማእከላቱ ያከናወኗቸው የዕቅድ ክንውን ዘገባዎች የቀረቡ ሲሆን፤ በዘገባዎቹ ላይ ውይይት እና አስተያየት ተሰጥቷል፡፡ በሌላ በኩል የማኅበሩን የአራት ዓመት ስልታዊ ዕቅድ መፈጸም ይቻል ዘንድ የማእከላቸውን ነባራዊ ሁኔታ ባማከለ የየራሳቸውን  ድርሻ በመውሰድ አጽድቀዋል፡፡

በአሰላ ማእከል ጠቅላላ ጉባኤ ላይ በመገኘት የማኅበረ ቅዱሳን መልእክት ያቀረቡት ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ስዩም ናቸው፡፡ ጠቅላላ ጉባኤው በተመረጡ የመወያያ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ውይይት አድርጓል፡፡ በመርሐ ግብሩ ላይ የወረዳ ማእከላት የልምድ ልውውጥ አካሂደዋል፡፡ የማእከሉ የ2005 ዓ.ም ሥራ እና የበጀት ዕቅድ ቀርቦ አሳብ ከተሰጠበት በኋላ ጸድቋል፡፡ በመርሐ ግበሩ ፈጻሜ ላይም ከዋና ማእከል የተገኘውን የንዋያተ ቅዱሳት እርዳታ ለገጠር አብያተ ክርስቲያናት ታድሏል፡፡

በተያያዘ ዜና፥ የአምቦ ማእከል የራሱን ጽሕፈት ቤት ለማስገንባት ያዘጋጀውን የመነሻ አሳብ፥ ጉባኤው ሰፊ ውይይት ካካሄደበት በኋላ፤ የቀረበውን አሳብ በማጽደቅ ዝርዝር አፈጻጸሙን የሥራ አስፈጻሚው እንዲመለከተው ወስኗል፡፡ በስልታዊ ዕቅድ ዘመኑም የግንባታው 5% ለመፈጸም መታቀዱን ከማእከሉ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡

debr 10

ደብረሊባኖስ ገዳምን የሚታደጉ ሰፋፊ ፕሮጀክቶችን ተግባራዊ ለማድረግ ሰፊ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑ ተገለጸ

ኅዳር 10 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ማለደ ዋስይሁን

 

debr 10

የደብረ ሊባኖስ ገዳምን በሁለንተናዊ መልኩ ለማሳደግ የሚያስችሉ ፕሮጀክቶች ተግባራዊ ለማድረግ እየተንቀሳቀሱ መሆኑን የገዳሙ ጸባቴ አባ ኃይለ መስቀል ውቤ አስታወቁ፡፡ ኅዳር 9 2005 ዓ.ም በማኅበረ ቅዱሳን ጽሕፈት ቤት ከገዳሙ ወዳጆች ጋር በተደረገው የምክክር መርሐ ግብር ላይ ይፋ እንደተደረገው ገዳሙ ያሉበትን ችግሮች ቀርፎ በቀጣይም አርአያ ምሳሌ ወደሚሆንበት ደረጃ የሚያደርሱትን እንቅስቃሴዎች ከማኅበረ ቅዱሳን ባለሙያዎች ጋር በመተባበር ለማከናወን መታቀዱን ጸባቴው ገልጸዋል፡፡

 

በዕለቱ በምክክር መርሐ ግብሩ የተገኙት፣ ገዳሙ የሚገኝበት ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ ገዳሙ በሁሉም ወገኖች ትኩረት ተነፍጎት የቆየ መሆኑን አውስተው በሀገሪቱ ታሪክ ውስጥ ከነበረው ዘርፈ ብዙ ሚናና ከታዋቂነቱ አንጻር ጠያቂ ተቆርቋሪ አጥቶ መኖሩ ሲያሳዝናቸው መቆየቱን አውስተዋል፡፡ በዕለቱም የማኅበረ ቅዱሳን ባለሙያዎች ገዳሙ አሁን ያለበትን ወቅታዊ ሁኔታ የሚያመለክት ጥናት በተለያዩ የመረጃ ማግኛ ዘዴዎች ተጠቅመው መሥራታቸው የተገለጸ ሲሆን የጥናቱም ውጤት ጠቅለል ብሎ በኢንጂነር ዮናስ ምናሉ እና በዶክተር ሳሙኤል ኃይለማርያም ቀርቧል፡፡

 

ወቅታዊ ሁኔታውን በማሳየት ሳያበቃም ወደፊት ተግባራዊ ለማድረግ ስለታሰቡት ፕሮጀክቶች ሰፊ ማብራሪያ ተሰጥቷል፡፡ ወደፊትም እያንዳንዱ ፕሮጀክት የሚጠይቀውን የገንዘብ፣ የሙያ፣ የሰው ኃይል ወዘተ ፍላጎት ባመላከተ ሁኔታ ተዘጋጅቶ እንደሚቀርብ የተገለጸ ሲሆን ሁሉም በምክክሩ ላይ የተሳተፉ የገዳሙ ወዳጆች ተግባሩ በመላው ሀገሪቱ ያሉ ምእመናንን ያሳተፈ ሆኖ በጥብቅና በጥልቅ ሁኔታ  መጀመር አለባቸው ሲሉ አሳስበዋል፡፡

 

በዕለቱ በተደረገውም ውይይት ተሳታፊዎች በገዳሙ ብዙ ፕሮጀክቶች ሲተገበሩ የገዳሙ አንገብጋቢ ችግሮች ቅድሚያ እንዲሰጣቸውና በየደረጃውም የገዳሙን ልዕልና የሚያስጠብቁና ምሳሌ የሚያደርጉትን ሌሎች ላቅ ያሉ ፕሮጀክቶች ወደመተግበር እንዲገባ ሲያሳስቡ ተስተውሏል፡፡ ይህንኑ በጎ ዓላማ ከግብ ለማድረስ የሚያነሣሣ የሕዝብ ጉባኤና የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር በታኅሣሥ 14 2005 ዓ.ም በዕለተ እሑድ ከጠዋቱ 3 ሰዓት ጀምሮ በጠቅላይ ቤተ ክህነት የስብከተ ወንጌል አዳራሽ ለማከናወን ዝግጅት እየተደረገ ነው፡፡ በጥሪው የሚሳተፉና በቅስቀሳውም የሚሰማሩ እጅግ በርካታ ወገኖች የሚጠበቁ ሲሆን ይህ የመጀመሪያው መርሐ ግብር እንደሆነም ተገልጿል፡፡

ቤተ ጣዖቱ ተዘጋ! የቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን የመሠረት ድንጋይ ተቀመጠ

ኅዳር 6 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

 

“በአርሲ ሀገረ ስብከት  በመርቲ ወረዳ ልዩ ስሙ ፈረቀሳ በተባለ ሥፍራ ከ120 አመታት በላይ የአርሲዋ እመቤት” በሚል የባዕድ አምልኮ ሥርዓት ሲፈጸምበት በነበረ ሥፍራ ላይ የባዕድ አምልኮ ሥርዓቱን በማጥፋት ብፁዕ አቡነ ናትናኤል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክና የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የቅዱስ ገብርኤልን ቤተ ክርስቲያን  ለመገንባት የመሠረት ድንጋይ ኅዳር 1 ቀን 2005 ዓ.ም. አኖሩ፡፡

 

ብፁዕነታቸው በሥፍራው ለተገኙት ምእመናን በሰጡት ቃለ ምዕዳን “ከዚህ በፊት ይህ ቦታ የአርሲዋ እመቤት በሚል የዲያቢሎስ መፈንጫ፡ የሕሙማን መዋያ የነበረ ሲሆን ከአሁን በኋላ ግን የምሕረትና የፈውስ አደባባይ እንዲሁም የእግዚአብሔር ድንቅ ሥራ የሚፈጸምበት ሆኗል” ብለዋል፡፡ ለአካባቢው ምዕመናን ባስተላለፉት መልዕክትም  የቤተ ክርስቲያኑን ግንባታ በአጭር ጊዜ ውስጥ በማጠናቀቅ የተጣለባቸውን ሓላፊነት ይወጡ ዘንድ አሳስበዋል፡፡

 

ይህ የባዕድ አምልኮ ሥርዓት ከ1885 ዓ.ም. ጀምሮ ወ/ሮ ሻበሻ ወርቅ ይመር በምትባል ሴት በሥፍራው እንደተመሠረተና ምዕመናንን በማሳሳት ከሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን እንዲያፈነግጡ በማድረግ እስካረፈችበት እሰከ ጥቅምት 19 ቀን 1912 ዓ.ም ድረስ ቆይታለች፡፡ ነገር ግን በወቅቱ ሲከተሏትና የመሠረተችውን የባዕድ አምልኮ ሥርዓት ሲያከናውኑ የነበሩ ተከታዮቿ  “የአርሲዋ እመቤት”፤ የአካባቢው ሙስሊሞች ደግሞ “ሞሚናት” በሚል አጠራር ሥርዓቱን በማጠናከር በዚሁ ቦታ ላይ በቅዱስ ገብርኤል ስም በየዓመቱ ጥቅምት 19 እና  ግንቦት 19 ቀን በከፍተኛ ሁኔታ የባዕድ አምልኮ ሥርዓቱን ለብዙ ዘመናት ሲያከናውኑት እንደቆዩ ይነገራል፡፡

 

የብዙ ዘመናት ጸሎት ሰምሮ በብፁዕ አቡነ ናትናኤል መመሪያ ሰጪነትና ድጋፍ ሀገረ ስብከቱና የወረዳው ቤተ ክህነት እንዲሁም ምእመናን ባደረጉት ጥረት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነትና ሥርዓት መሠረት ባዕድ አምልኮ መፈጸም የተወገዘ መሆኑን በማስተማርና በማሳመን የመሠረት ድንጋዩ እንዲቀመጥና የቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን እንዲሠራ ስምምነት ላይ ተደሷርል፡፡

 

በአካባቢው የሚገኙ የእስልምና እምነት ተከታዮችም የእርሻ ማሳቸውን ለቤተ ክርስቲያን መሥሪያ በመፍቀድ ከ1200,00 ብር በላይ በማዋጣት መለገሳቸውን የደረሰን ዘገባ ያመለክታል፡፡

ማኅበሩ የነጻ የትምህርት ዕድል መስጠት ሊጀምር ነው፡፡

ኅዳር 5 ቀን 2005 ዓ.ም.

ዲ/ን ቴዎድሮስ ኃይሉ

 

ማኅበረ ቅዱሳን ኅዳር 2 ቀን 2005 ዓ.ም ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች፣ የሰንበት ትምህርት ቤት ተወካዮችና የማኅበረ ቅዱሳን አባላት በተገኙበት በጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ በተደረገ የማስተዋወቂያ መርሐ ግብር ለአብነት ተማሪዎችና መምህራን የነጻ ትምህርት ዕድል ለመስጠት መዘጋጀቱን ገለጸ፡፡

 

በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ማኔጂንግ ዳይሬክተር ዲ/ን አዕምሮ ይኄይስ “ማኅበሩ ሐምሌ 21/2004 ዓ.ም በአዲስ አበባ ግዮን ሆቴል ከአብነት ምስክርና ከዩኒቨርስቲ ምሁራን ጋር የዘመናዊውን ትምህርት ከአብነት ትምህርት ጋር አቀዳጅቶ የመስጠትን አስፈላጊነት ወሳኝ ውይይት አድርጎ፤ በአባ ጊዮርጊስ ስም የተሰየመ ነጻ የትምህርት ዕድል ማዘጋጀቱን” ገልጸዋል፡፡

 

የአብነት ትምህርት ማጠናከሪያ፣ ማቋቋሚያና የአባ ጊዮርጊስ የነጻ ትምህርት ሥልጠና ዕድልን በተመለከተ አጠቃላይ ገለጻ ያደረጉት፤ የቅዱሳት መካናትና ልማት የቦርድ ሰብሳቢ ወ/ሮ ዓለም ፀሐይ “የመርሐ ግብሩ ዓላማ የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች ዘመኑን በዋጀ መልኩ ተጽዕኖ ፈጣሪ የሚያደርጋቸው ነው” ብለዋል፡፡ እንደ ወ/ሮ ዓለም ፀሐይ ገለጻ የአባ ጊዮርጊስ ነጻ ትምህርት ዕድል የአብነት ትምህርት ተማሪዎችና መምህራን ከመለስተኛ ደረጃ እስከ ከፍተኛ የዘመናዊ ትምህርት ወይም ሥልጠና እንዲያገኙ የሚያግዝ ዕቅድ ነው፡፡ አክለውም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን የአብነት ትምህርት ቤቶች ከዘመናዊው ትምህርት ጋር አብሮ አላደገም ያሉት ወ/ሮ ዓለም ፀሐይ በዚህም እነዚህ ትምህርት ቤቶች ያለተንከባካቢና ከመንግሥት የሚደረገው ድጎማ መቅረቱ ሊቃውንቱ ያለተተኪ እንዲቀሩ አድርጓቸዋል፤ በዚህም ገዳማት ችግር ላይ መውደቃውቸን ተናግረዋል፡፡ አያይዘውም የአብነት ትምህርት እንደ ዕውቀት ተመራጭ አለመሆኑ፣ የአብነት ትምህርት ውሱንነት፣ በአብነት ትምህርት ለተማሩ አማራጭ የሥራ ዕድል አለመኖሩና ዘመኑን በዋጀ ሁኔታ በየደረጃው በበቂ ዕውቀት የሚያገለግሉ ካህናት ማነስን እንደ ችግር የጠቀሱት ወ/ሮ ዓለም ፀሐይ፤ ይህ መርሐ ግብር ለቤተ ክርስቲያን የአብነት ትምህርት ቤቶች የሰው ኀይል ምንጭ በመሆናቸው አስፈላጊ ነው ብለዋል፡፡

 

መርሐ ግብሩ በ750 ተማሪዎች ለሁለት ዓመት በሚቆይ የሙከራ ጊዜ የሚጀመር ሲሆን በዓመት እስከ አምስት ሚሊዮን ብር የሚጠይቅና በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገር የሚገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናን የገንዘብ ምንጭ መሆናቸውን እንዲሁም በጥር 2005 ዓ.ም እንደሚጀመር ለማወቅ ተችሏል፡፡