ታህሣሥ 6 ቀን 2005 ዓ.ም ምሽት ላይ በአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ የአማርኛ ፕሮግራም ዲ/ን ዓባይነህ ካሴ የተሰጡት ቃለ ምልልስ ማኅበሩን የማይወከል መሆኑን ስለማሳወቅ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ። አሜን።
በማኅበረ ቅዱሳን ያላቸውን ሓላፊነት በመጥቀስ ዲ/ን ዓባይነህ ካሴ ታህሣሥ 6 ቀን 2005 ዓ.ም ምሽት ላይ በአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ የአማርኛ ፕሮግራም ለቃለ ምልልስ ቀርበው  በወቅታዊው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጉዳዮች ላይ ሓሳብ መስጠታቸው ይታወሳል።  ማኅበረ ቅዱሳንን በመወከል  ለመገናኛ ብዙኃን መግለጫም ሆነ ቃለ ምልልስ መስጠት የሚችሉት የማኅበሩ ሰብሳቢ ወይም ዋና ጸሐፊ ወይም የማኅበሩ ሕዝብ ግኑኝነት ሓላፊ ናቸው፡፡ ስለዚህ  ዲ/ን ዓባይነህ ካሴ  በቃለ ምልልሳቸው የሰጡት አስተያየት የግል አስተያየታቸው መሆኑን በአክብሮት  እንገልፃለን።

ረድኤተ እግዚአብሔር አይለየን
የማኅበረ ቅዱሳን ጽ/ቤት
ታህሣሥ 12 ቀን 2005 ዓ.ም
አዲስ አበባ

“ወበ እንተዝ ኢየኃፍር እግዚአብሔር ከመ ይትበሃል አምላኮሙ” (ክፍል 2)

ታኅሣሥ 10 ቀን 2005 ዓ.ም.

በቀሲስ ይግዛው መኰንን

4.    ሰማያዊውን ሕይወት ናፋቂዎች ስለሆኑ

ክቡር ዳዊት “በቤትህ የሚኖሩ ሁሉ የተመሰገኑ ናቸው፤ ለዓለምና ለዘለዓለምም ያመሰግኑሃል፡፡ አቤቱ እርዳታው ከአንተ ዘንድ የሆነለት በልቡም የላይኛውን መንገድ የሚያስብ ሰው ምስጉን ነው፡፡” በማለት ሰማያዊውን መናፈቅ እንደሚያስመሰግን በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝቶ ተናገረ፡፡ መዝ. 83፥4 ቅዱስ ጳውሎስም የሚጠበቅበትን አገልግሎት ካከናወነ በኋላ “ልሄድ ከክርስቶስም ጋር ልኖር እናፍቃለሁ፤ ከሁሉ ይልቅ እጅግ የሚሻል ነውና፤” በማለት ምድራዊ ያይደለ ሰማያዊ ሕይወት ምን ያህል እንደሚናፈቅ ገልጿል፡፡ ፊል.1፥23 ለዚህ ነው ቅዱሳን በሥጋ የምኞት ፈረስ እንዲጋልቡ፥ በኀጢአት ባሕር እንዲዋኙ፥ በክፉ አሳብ ጀልባ እንዲቀዝፉ የሚፈታተናቸውን ርኩስ መንፈስ በመልካም ሥራቸው በመቃወም ድል የሚያደርጉት፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ “ለእኛም ይገለጥ ዘንድ ካለው ክብር ጋር ቢመዛዘን የአሁኑ ዘመን ሥቃይ ምንም እንዳይደለ አስባለሁ፡፡” በማለት የአሁኑን ችግርና ፈተና ከሚመጣው ጋር በማመዛዘን የተናገረው፡፡ ሮሜ.8፥18

 

ቅዱስ ኤፍሬምም በውዳሴ ማርያም ጸሎቱ “ሰማዕታት በእውነት የዚህን ዓለም ጣዕም ናቁ፤ ስለ እግዚአብሔርም ሲሉ ደማቸውን አፈሰሱ፤ ስለመንግሥተ ሰማያትም ሲሉ መራራ ሞትን ታገሡ፡፡” በማለት የዚህን ዓለም መከራ መታገሥ ሰማያዊውን ክብር በማስታወስና የሚገኘውን ዋጋ በማመን እንደሆነ ገልጿል፡፡ /የሐሙስ ውዳሴ ማርያም/ ለዚህም ነው ሰማእታት እሳቱን ስለቱን፣ ጻድቃን ግርማ ሌሊቱን፥ ጽምፀ አራዊቱን፣ ጸብአ አጋንንቱን ታግሰው ሥጋቸውን ለነፍሳቸው አስገዝተው የኖሩበት ዐቢይ ምሥጢር፡፡ ሰማዕታት የሚታሰሩበትን ገመድ፣ የሚሰቀሉበትን ግንድ ይዘው ወደ ሞት ሲነዱ ጻድቃንም አስኬማቸውን ደፍተው፣ ደበሎአቸውን ለብሰው፣ ከምግበ ሥጋ ተለይተው ርሃቡን ጥሙን ችለው ሲኖሩ ደስ ይላቸዋል፡፡ ምክንያቱም ከፈጣሪያቸው እንደሚያገኙ ያውቃሉና ነው፡፡ መሬት ፊቷን ወደ ፀሐይ ስታዞር ብርሃን እንደምታገኝ፣ ፊቷን ስትመልስ ደግሞ ጨለማ እንደሚሆን ሳይንሱ ይነግረናል፡፡ የሰው ልጅም ፊቱን ወደ እግዚአብሔር ካዞረ ብርሃን ይሆንለታል፤ ፊቱን ከፈጣሪው ካዞረ ግን ይጨልምበታል፡፡ ኑሮው፣ ትዳሩ፣ መንገዱ ሁሉ የተሳካ እንዲሆን፣ የውስጥ ሰላምን እንዲያገኝ፣ በሚያገኘው ተደስቶ እንዲኖር፣ ሰላም፣ ጤና በረከት ከቤቱ እንዳይርቁ፣ አሸሼ ገዳሜ በሉ፣ አይዟአችሁ ጨፍሩ የሚለውን የጥንት ጠላት የአጋንንት ስብከት በመልካም ሥራ በዝማሬ በማኅሌት በሰዓታት በቅዳሴ፣ በኪዳን ተጠምዶ መቃወም ያስፈልጋል፡፡ መቼም የሰይጣን የዘወትር ስብከት “ሥጋችሁ በነፍሳችሁ ላይ ትንገሥ” የሚል ስለሆነ እኛ ግን ነፍሳችንን በሥጋችን ላይ ልናነግሣት እንደ አባቶቻችን ቅዱስን ሰማያዊውን ናፋቂዎች ልንሆን ያስፈልጋል፡፡ “ድንኳን የሚሆነው ምድራዊ መኖሪያችን ቢፈርስ በሰማይ ያለ በእጅ ያልተሠራ የዘለዓለም ቤት የሚሆን ከእግዚአብሔር የተሠራ ሕንፃ እንዳለን እናውቃለንና፡፡ በዚህ ውስጥ በእውነት እንቃትታለንና፣ ከሰማይም የሚሆነውን መኖሪያችንን እንድንለብስ እንናፍቃለንና ለብሰን ራቁታችንን አንገኝም፡፡” እንዲል፡፡ 2ቆሮ.5፥1

 

5.    ለሌላው አሳቢዎች በመሆናቸው

ለሌላው ማሰብ፥ ለሌላው መጨነቅ፥ ከሚደሰቱ ጋር መደሰት፥ ከሚያዝኑ ጋር ማዘን፥ ችግር የወደቀባቸውን ሰዎች የችግራቸው ተካፋይ መሆን ፈጣሪን መምሰል ነው፡፡ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ “በአንድ አሳብ ተስማሙ፣ አንድ ፍቅር፣ አንድም ልብ፣ አንድም አሳብ ይሁንላችሁ፤ ለወገኔ ይጠቅማል በማለት ወይም በከንቱ ውዳሴ ምክንያት አንድ እንኳ አታድርጉ፤ ነገር ግን እያንዳንዱ ባልንጀራው ከራሱ ይልቅ እንዲሻል በትሕትና ይቁጠር፤ እያንዳንዱ ለራሱ የሚጠቅመውን አይመልከት፡፡ ለባልንጀራው ደግሞ እንጂ፡፡ በክርስቶስ ኢየሱስ የነበረ ይህ አሳብ በእናንተ ዘንድ ደግሞ ይሁን፡፡” በማለት ከራስ ይልቅ ለሌላው ማሰብን እንድናስቀድም ያስተምረናል፡፡ ፊልጰ.2፥1 ታላቁ ሊቅም በሰቆቃወ ድንግል ላይ “ኢየሱስ ስዱድ ተስፋሆሙ ለስዱዳን፡፡ ኢየሱስ ግፉዕ ምስካዮሙ ለግፉዓን፡፡ እግዚአብሔር ማኅደር ዘአልቦ ከመ ነዳያን..” በማለት የጌታችን መሰደድ የተሰደደውን የሰውን ልጅ ለመመለስ እንደሆነ፤ ጌታችን ያለ በደሉ የተገፋው የተገፋ የሰውን ልጅ ሊያድን እንደሆነ፤ እግዚአብሔር ተስፋ፣ ላጡ ተስፋ ማረፊያ ቤት ለሌላቸው ማረፊያ እንደሆነ ይነግረናል፡፡ ይህንን ስለሚያውቁ ቅዱሳን ከራሳቸው በላይ ለሌላው ያስባሉ፡፡ “ይህንን ኀጢአታቸውን ይቅር በላቸው፤ ያለዚያ ግን ከጻፍኸው መጽሐፍ እባክህ ደምስሰኝ አለ፡፡” የሚለውን የታላቁን ሰው የሙሴን ልመና ስንመለከት ምን ያህል ለሌላው ማሰብ እንደሚገባ እንማራለን ዘፀ.32፥32 ዛሬ ቢሆን ምናልባት ሌላውን ደምስሰህ እኔን ጻፍ ሳይባል ይቀራል ትላላችሁ፡፡ ቅዱሳን ግን እንደፈጣሪያቸው ለሌላው አሳቢወች በመሆናቸው “እግዚአብሔር አያፍርባቸውም” ተባለ፡፡

 

ዛሬም ሰው ለድሃ እጁን ሲዘረጋ እግዚአብሔር ደግሞ የምሕረት እጁን ይዘረጋለታል፡፡ የወደቀ ባልንጀራውን ሲያነሣ እግዚአብሔር እርሱን ከወደቀበት ያነሣዋል፡፡ የተጨነቀውን ሲያጽናና፥ የተጨቆነውን ነጻ ሲያወጣ ተስፋ ለቆረጠው ሲደርስለት በእውነት ዋጋው አይጠፋበትም፡፡ ለዚህ ነው ክቡር ዳዊት “ለችግረኛና ለምስኪን የሚያስብ ምስጉን ነው፤ እግዚአብሔር ይጠብቀዋል፤ ሕያውም ያደርገዋል፡፡” በማለት ያስተማረን፡፡ መዝ. 40፥1 ስለዚህ በዘመናችን ያለውን የወገንተኝነት፥ የትዕቢትና የሥጋዊነትን አስተሳሰብና አመለካከት በወንጌል መሣሪያነት አፈራርሶና ንዶ ለራስ ነጻ በመውጣት ለሌላውም መትረፍ ያስፈልጋል፡፡ ከነዚህ ክፉ ተግባራት ካልተለየን ገና ዛሬም በጨለማ ውስጥ ስላለን እንጠንቀቅ፡፡

 

“ልጄ ድሃውን ምጽዋቱን አትከልክለው ከሚለምንህ ከድሃውም ዓይኖችህን አትመልስ፡፡ የተራበች ሰውነትን አታሳዝን ያዘነ ሰውንም አታበሳጭ፡፡ ያዘነ ልቡናን አታስደንግጥ፣ የሚለምንህን ሰው አልፈኸው አትሂድ፡፡ የሚገዛልህ ቤተ ሰብህን አትቆጣ፤ ከድሃም ፊትህን አትመልስ፡፡” ካለ በኋላ ቀጥሎ “ከሚለምንህ ሰው ፊትህን አትመልስ፤ በልቡናው አዝኖ ቢረግምህ ፈጣሪው ልመናውን ይሰማዋልና፡፡” በማለት ምስካየ ኅዙናን፣ ረዳኤ ምንዱባን የሆነ እግዚአብሔር የድሃውን ኀዘን ሰምቶ እንደሚበቀል ይነግረናል፡፡ ሲራ.4፥2 ስለዚህ የነዚህ ቅዱሳን ልጆች የሆን እኛ ፍትሕ ተጓድሎባቸው የሚሰማቸው አጥተው የሚገባቸውን፣ ተነፍገው፣ መከበር ሲገባቸው ተዋርደው ከሰው በታች ሆነው ለሚቆዝሙ ወገኖች ፈጥነን ልንደርስላቸው ይገባል፡፡ “ሳትሞት ለባልንጀራህ በጎ ነገርን አድርግ፡፡” ተብለን ተመክረናልና፡፡ ሲራ.14፥13

 

6.    ለመከራ ራሳቸውን ያዘጋጁ በመሆናቸው

ከላይ እንዳየነው እምነታቸው በማዕበል ቢመታ የማይፈርስ እውነተኛ እምነት ስለሆነ ለመከራ አይበገሩም፡፡ ከእሳቱ ከሰይፉ ከመከራው በስተጀርባ የሚወርድላቸው አክሊለ ሕይወት ስለሚታያቸው ወደሞት ሲነዱ ደስ እያላቸው ይሄዳሉ፡፡ ራሳቸውን ለሞት ራሳቸውን ለስቅላት፣ ራሳቸውን ለእንግልት አዘጋጅተው በሃይማኖት ስለሚኖሩ፣ ፈጣሪ ያዝንላቸዋል፡፡ ደስ ይሰኝባቸዋልም፡፡ ያለ መከራ ዋጋ እንደማይገኝም ስለሚያውቁ “አቤቱ ቅጣኝ ነገር ግን እንዳታዋርደኝ በመጠን ይሁን እንጂ በቁጣ አይሁን፡፡” እያሉ ድሎትን ሳይሆን መከራ ሥጋን ይለምናሉ፡፡ ኤር.1፥24 ሥጋ ሲጎሰም ለነፍስ እንደሚገዛ ይረዳሉ፡፡ “ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል መከራ ወይስ ጭንቀት ወይስ ስደት፣ ወይስ ረሃብ ወይስ ራቁትነት፣ ወይስ ፍርሃት፣ ወይስ ሰይፍ ነውን “ስለ አንተ ቀኑን ሁሉ እንገደላለን፣ እንደሚታረዱ በጎች ተቆጥረን” ተብሎ እንደተጻፈ ነው፡፡ በዚህ ሁሉ ግን በወደድን በእርሱ ከአሸናፊዎች እንበልጣለን፡፡ ሞት ቢሆን፣ ሕይወትም ቢሆን፣ መላእክትም ቢሆኑ ግዛትም ፍጥረትም ቢሆን፣ በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን ካለ ከእግዚአብሔር ፍቅር ሊለየን እንዳይችል ተረድቼአለሁ፡፡” የሚለው የቅዱስ ጳውሎስም ትምህርት የሚያስተምረው ራስን ለመከራ ማዘጋጀትን ነው፡፡ ሮሜ.8፥35

 

ገበሬ ብርዱን፣ ዝናቡን፣ ፀሐዩን ታግሦ እሾሁን ነቅሎ መሬቱን አለምልሞ ተክል የሚተክለውና ከበቀለም በኋላ የሚኮተኩተው የሚያርመው ፍግ እያስታቀፈ የሚንከባከበው ውኃ እያጠጣ፣ ፀረ ተባይ መድኀኒት እየረጨ ከተባይ የሚጠብቀው፣ ቅጥር ምሶለት፣ አጥር አጥሮለት ከእንስሳት የሚያስጠብቀው በአጠቃላይ ብዙ የሚደክምለት መልካም ፍሬን  ለማግኘት ነው፡፡ እንዲህ ከለፋ በኋላ አመርቂ ውጤት ቢያገኝ በልፋቱ ይደሰታል፡፡ በሚቀጥለውም ከመጀመሪያው የበለጠ እንክብካቤ ያደርግለታል፡፡ ካልሆነ ግን ያዝናል፡፡ ተክሉ ፍሬ አልባ ቢሆን ወይም ደግሞ ጣፋጭ ፍሬን እየጠበቀ መራራ ፍሬን ቢያፈራ ከማዘንም አልፎ እንዲቆረጥ ያደርገዋል፡፡ ዮሐ.15፥5፣ ማቴ.21፥18

 

ሰውም የእግዚአብሔር ተክል ነው፡፡ በቃለ እግዚአብሔር በምክረ ካህን ተኮትኩቶ በረድኤተ እግዚአብሔር አጥርነት ተጠብቆ የሚኖር የእግዚአብሔር የእጁ ሥራ ነው፡፡ ታዲያ ይህንን ስለሚያውቁ ቅዱሳን መልካም ፍሬን አፍርተው በመገኘታቸው እግዚአብሔር ተደስቶባቸዋል፡፡

 

ፍሬአቸው መራራ የሆኑ ተክሎች /ሰዎች/ ጨለማን ተገን አድርገው ሰው አየን አላየን ብለው ኀጢአትን የሚፈጽሙትን ያህል በእግዚአብሔር ቤት የተተከሉ፣ ፍሬአቸው ያማረ ቅዱሳን ጨለማው ሳይከለክላቸው ጽድቅን ሲሠሩበት ያድራሉ፡፡ በዓለም ላይ ለ5 ሲሕ 5 መቶ ዘመናት ኀጢአት በዓለም ላይ ነግሦ ይኑርም እንጂ በዚህ ኀጢአት በነገሠበት ዘመን ጽድቅን ሲሠሩ የኖሩ አባቶችና እናቶች ነበሩ፡፡ ዛሬም ኀጢአት በዓለማችን ላይ ጠፍንጎ ይዞ እያስጨነቀን እንዳለ ብንረዳም የነዚህ የቅዱሳን አበው በረከት ያደረባቸው በየገዳማቱ ወድቀው ለጽድቅ ራሳቸውን ሲያስገዙ እንመለከታለን፡፡

 

ማጠቃለያ

አንድን መንፈሳዊ ሥራ መጀመር ብቻውን የጽድቅ ምልክት አይደለም፡፡ ከላይ ያየናቸው የቅዱሳን ሕይወት ጽድቃቸው ከሰውም አልፎ በእግዚአብሔር የተመሰከረላቸው ከመጀመሪያው ይልቅ መጨረሻቸው በማማሩ ነው፡፡ ጀምረው ያቋረጡማ የሚነገርላቸው ማቋረጣቸው እንጂ ጽድቃቸው አይደለም፡፡ እንደሚታወቀው ሳጥናኤል የመላእክት አለቃ ነበር፡፡ አርዮስ ካህን፣ ይሁዳ ከሐዋርያቱ ጋር ተቆጥሮ የነበረ፣ ዴማስ ከአርድዕተ ክርስቶስ ከነ ሉቃስ ጋር ተደምሮ የነበረ እንደሆነ እናውቃለን፡፡ ታዲያ እነዚህ ሰዎች የጀመሩትን መንፈሳዊ አገልግሎት ችላ ማለታቸው ከሰማይ ወደ ምድር፣ ከክብር ወደ ውርደት፣ ከሹመት ወደ ሽረት፣ ከማግኘት ወደ ማጣት ተወረወሩ እንጂ ምን ጠቀማቸው? በትናንት ማንነት ብቻ ድኅነት አይገኝም፡፡ ዛሬ የማያሳፍር ሥራን መሥራት እንጂ፡፡

 

ትናንት ዘመነኞች፣ ቅንጦተኞች፣ ኩሩዎች፣ የነበሩ ነገሥታት ወመኳንንት ዛሬ የት አሉ? በሀብታቸው የሚኩራሩ፣ በሥልጣናቸው የሚንጠራሩ፣ ፊታቸውን ከፈጣሪ ያዞሩ ሁሉ ጊዜ አልፎባቸው ገንዘባቸው፣ ሥልጣናቸው፣ ወገናቸው አላድናቸው ብሎ በጸጸት አለንጋ ከመገረፍ ውጪ ምንም አላገኙም፡፡ ስለዚህ ከዚህ መማር የዘመኑ ትውልድ ድርሻ ነው፡፡ በሃይማኖት ቁመው ከተጠቀሙት በሃይማኖት የመቆምን ጥቅም፣ ወድቀው ከተጎዱት የመውደቅን አስከፊነትና ጉዳት መማር እንችላለን፡፡ ስለዚህ ቆም ብለን ራሳችንን እንመርምር፡፡ በየመሥሪያ ቤታችን የምንሠራው ሥራ ሰውንና እግዚአብሔርን የሚያስደስት ነው ወይስ የሚያሳዝን፣ በአርአያውና በአምሳሉ ፈጥሮ በተለይ በሐዲስ ኪዳን “ከአሁን በኋላ ባሮች አልላችሁም፣ ልጆች ብያችኋለሁ፡፡” በማለት ያቀረበውን ፍጹምም የወደደውን የሰው ልጅ እንዴት እያየነው ነው? እውነት የምንሠራው ሥራ አሳፋሪ ነው ወይስ የሚያስደስትና የሚያስከብር? የሚለውን ጠይቀን ለራሳችን ምላሽ ልንሰጥ ያስፈልጋል፡፡ ያለ እግዚአብሔር መልካም ፈቃድ መልካምን ማድረግም አይቻልምና ለመልካም ሥራ እንዲያነሣሣን ኃይሉን ብርታቱንም እንዲሰጠን መልካም ፈቃዱ ይሁንልን፡፡

yaba gy. 7

ለሁለንተናዊ የቤተ ክርስቲያን እድገት የገዳማት ድርሻለሁለንተናዊ የቤተ ክርስቲያን እድገት የገዳማት ድርሻ

ታኅሣሥ 8 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

ሪፓርታዥ

yaba gy. 7የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ተልእኮ ለማሳካት የገማት ድርሻ በሚል መሪ ቃል ማኅበረ ቅዱሳን ባዘጋጀው ዐውደ ጥናት ላይ ለመገኘት ከ65 ገዳማት የመጡ አበምኔቶችና እመምኔቶች ቅዳሜ ታኅሣሥ 6 ቀን 2005 ዓ.ም. ጠዋት በማኅበሩ ሕንጻ  ላይ ስለ ማኅበሩ ሰፋ ያለ ግንዛቤ እንዲኖራቸው ለማስቻል በተዘጋጀው መርሐ ግብር ውይይት ሲያደርጉ ቆይተዋል፡፡

 

ከስዓት በኋላ  በዐውደ ጥናቱ ላይ ለመገኘት በተዘጋጀላቸው መኪና ከማኅበሩ ዋና ጽሕፈት ቤት ወደ ኢትዮጵያ ስብሰባ ማእከል አዳራሽ ያመሩ ሲሆን ኢትዮጵያ ስብሰባ ማእከል እንደደረሱ በማኅበረ ቅዱሳን መዘምራን በዝማሬ በመታጀብ ወደ አዳራሹ ገብተዋል፡፡ በአዳራሹ ውስጥ የተገኙ ምእመናን በእልልታና ዝማሬ አቀባበል በማድረግ ገዳማውያን አባቶችም እጅ እየነሱና ምእመናን እየባረኩ ወደ ተዘጋጀላቸው ቦታ በማምራት ቦታቸውን ያዙ፡፡

 

yaba gy 1የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ዐቃቤ መንበር ብፁዕ አቡነ ናትናኤል ከብፁዐን ሊቃነ ጳጳሳት ጋር በመሆን  እንደተገኙም ዐውደ ጥናቱ ተከፍቷል፡፡

 

የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ ቀሲስ ዶ/ር ሰሙ ምትኩ የእንኳን ደኅና መጣችሁ መልእክታቸውን ለማስተላለፍ መድረኩን የተረከቡ ሲሆን በመልእክታቸውም ማኅበረ ቅዱሳን በኢትዮጵያ ጥንታዊ ገዳማት ላይ እየደረሰ ያለውን ልዩ ልዩ ችግሮች ለመታደግና የበኩሉን ድርሻ ለመወጣት ጥረቶችን በማድረግ ላይ እንደሚገኝ የገለጹ ሲሆን ገዳማትና የአብነት ትምህርት ቤቶች ያሉባቸውን ሁኔታ ለማጥናትና አግባብ ያለው መፈትሔ ለመስጠት መርሐ ግብር ነድፎ ተግባራዊ ሲያደርግ መቆየቱን ተናግረዋል፡፡

 

እስካሁን ከ100 በላይ ፕሮጀክቶች የተተገበሩና በመተግበር ላይ እንደሚገኙ የገለጹት ስብሰቢው በ145 አብነት ትምህርት ቤቶች ለ136 መምህንና ለ988 የአብነት ተማሪዎች ቋሚ ወርኀዊ የገንዘብ ድጋፍ ያደርጋል ብለዋል፡፡ ለገዳማት አበምኔቶችና እመምኔቶች ጥሪ የተደረገበትንም ምክንያት ሲገልጹ “ገዳማት ራሳቸውን እንዲችሉ በሚደረገው ጥረት ንቁ ተሳታፊ እንዲሆኑ ማስቻል፤ ገዳማት ከገዳማት ጋር ያላቸውን ትሥሥር ለማጠናከርና ወሳኝ አቅጣጫዎችን ለማስያዝ ከገዳማት አባቶች ጋር መመካከርና መወያያት አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ ማኅበሩ ጥሪ አድርጓል” ብለዋል፡፡

 

ገዳማውያን አባቶችም ጥሪውን ተቀብለው አስቸጋሪውን ጉዞ ሁሉ ተቋቁመው በመገኘታቸው ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

 

በቀጣይነት የቀረበው በቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ስዮም ለሁለንታናዊ የቤተ ክርስቲያን እድገት የገዳማት ድርሻ በሚል ርእሰ ጉዳይ ላይ በመመርኮዝ “የገዳማት መጠናከር ለቤተ ክርስቲያን እድገት ያለው ሚና ምንድን ነው?” በሚል ጥናታቸውን አቅርበዋል፡፡ በጥናታቸውም ከዳሰሷቸው መካከል

 

  • ገዳማት የቤተ ክርስቲያናችን ሥውር ጓዳዎችና የምስጢር መዝገቦች ናቸው፡፡

  • ገዳማት የመማጸኛ ከተሞች ናቸው፡፡

  • ታላላቅ የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት የተገኙባቸው ምንጮች ናቸው

  • የተግባራዊ ክርስትና ሞዴሎች ናቸው

  • ገዳማውያን ለእግዚአብሔር የሚቀርቡ አሥራት በኩራት ናቸው፡፡

  • ገዳማት የብዝሃ ሕይወት መገኛና መጠበቂያ ናቸው፡፡

  • ለሁለንተናዊ የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት መሠረት ናቸው

  • የማኅበራዊ ደኅንነት አገልግሎት መሥጫ ሥፍራዎች ናቸው፡፡

 

በማለት ሰፊ ትንታኔ በመስጠት ገዳማት ለቤተ ክርስቲያን እድገት አስፈላጊ መሆናቸውውን አብራርተዋል፡፡

 

በተያዘው መርሐ ግብር መሠረት በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ መምህር የሆኑት ፕሮፌሰር ሺፈራው በቀለ በኢትዮጽያ ገዳማት ላይ ያደረጉትን ጥናት አቅርበዋል፡፡ በጥናታቸውም ለኢትዮጵያ ሥልጣኔ ገዳማት ያላቸው ሚናና እነዚህንም የሥልጣኔ ምንጮቻችንን ጥበቃ ማድረግ እንደሚገባ ትኩረት ሰጥተው አብራርተዋል፡፡

 

በኢትዮጵያ ጥንታዊ ገዳማት ውስጥ ከ1500 በላይ ዘመናት ያስቆጠሩ የብራና መጻሕፍት መኖራቸውና በምሳሌነትም በአባ ገሪማ ገዳም የሚገኘውን የብራና ወንጌልን ጠቅሰዋል፡፡ በተጨማሪም በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሚገኙ ጥንታዊ ሥዕላትና ረጅም ዘመናትን ያስቆጠሩ ቤተ ክርስቲያናትና የአብነት ትምህርት ቤቶች ሳይፈርሱ በቅርስነት መያዝ እንደሚገባቸው ገልጸዋል፡፡

 

yaba gy. 739በጥናታቸው ማጠቃለያም “እነዚህ ቅርሶች የእኛ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፤ የሁላችንም የኢትዮጵያውን /ሃይማኖታችን ምንም ቢሆን/፤  የመላው ጥቁር ሕዝቦች እንዲሁም  የሰው ልጆችና የዓለማችን ቅርሶች ናቸው፡፡ ጥቁር ሕዝቦች እጅግ የረዘመ የሥእልና የኪነ ጥበብ ቅርስ የላቸውም የሥእልና የኪነ ጥበብ ቅርስ ያለው ሕዝብ እኛ ኢትዮጵያውያን ነን፡፡ እነዚህን ቅርሶች ያቆየችልን ደግሞ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ናት” ብለዋል፡፡

 

ጥናቱ እንደተጠናቀቀ ማኅበረ ቅዱሳን በገዳማት ውስጥ እያከናወናቸው ከሚገኙ ተግባራት መካከል ለምሳሌነት የቀረቡ ገዳማትን በመጥቀስ የባሌ መካነ ሕይወት አቡነ ተክለ ሃይማኖት ገዳም፣ የአቃቂ ደብረ ገነት አባ ሳሙኤል ቤተ ደናግል ገዳም፣ የምድረ ከብድ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም አበምኔቶችና እመምኔት ከማኅበረ ቅዱሳን ጋር ያከናወኑትን ሥራ አቅርበዋል፡፡ በተጨማሪም በትግራይ ክልል የሚገኙትን ገዳማት በመከታተል ከፍተኛ አገልግሎት እያበረከተች የምትገኘው ጸጋ ኪሮስ ግርማይ ሪፖርት አቅርባለች፡፡

 

የባሌ መካነ ሕይወት አቡነ ተክለ ሃይማኖት ገዳም መጋቢ አባ ክንፈ ገብርኤል “ማኅበረ ቅዱሳን ወደ ገዳማችን በመምጣትና ችግራችንን በማየት ባጠናው ጥናት መሠረት የከብት እርባታ ለመጀመር የሚያስችለን ፕሮጀክት በመንደፍ 2 የወተት ላሞችን ሰጥቶን ሥራችንን ጀመርን፡፡ ዛሬ 24 ደርሰውልናል፡፡ 27 ደግሞ ሸጠን ተጠቅመናል፡፡ 18 ሞተውብናል፡፡ ተጨማሪ ሥራዎችንም በመሥራት ላይ እንገኛለን፡፡ ውጤታማም ሆነናል” ብለዋል፡፡

 

ከአቃቂ ደብረ ገነት አባ ሳሙኤል ቤተ ደናግል የገዳሙ እመ ምኔት እማሆይ መብዐ ጽዮን ማኅበሩ ስላደረገላቸው ድጋፍ ሲገልጹ “አንድ የልብስ ስፌት መኪና፤4 ጣቃ ጨርቅ እንዲሁም 2 ላሞችን ሰጥቶን ሥራችንን የጀመርን ሲሆን ዛሬ 10 የወተት ላሞች አድርሰናል” ብለዋል፡፡ በተጓዳኝም 10 ሕጻናትንም እያሳደጉ እንደሚገኙ ገልጸዋል፡፡

 

yaba gy 6የማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ከገዳማት ጋር ባደረገው የተቀራረበ ሥራ ከ1992 ዓ.ም. ጀምሮ ከፍተኛ አፈጻጸም ላሳዩ ገዳማት የዋንጫ ሽልማት  ማበርከቱ አንዱ የመርሐ ግብሩ አካል ነበር፡፡ ለሽልማት የበቁትም የባሌ መካነ ሕይወት አቡነ ተክለ ሃይማኖት ገዳም፣ የአቃቂ ደብረ ገነት አባ ሳሙኤል ቤተ ደናግል ገዳምና የደቡብ ጎንደር ገዳመ ኢየሱስ የተዘጋጀላቸውን ሽልማት ተቀብለዋል፡፡

 

በዐውደ ጥናቱ ላይ ከቀረቡት መርሐ ግብሮች መካከል የአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ እና የአባ በጸሎተ ሚካኤል ገድል ምረቃ ሲሆን ከምረቃው በፊት በገድሉ ዙሪያ አጭር ትንታኔ በማኅበረ ቅዱሳን የኤሌክትሮኒክስና ሚዲያ የቴሌቪዥን ክፍል አስተባባሪ በዲያቆን ሄኖክ ኀይሌ ተሰጥቷል፡፡

 

የአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ገድል ለመተርጎም ከሦስት ዓመታት በላይ መውሰዱንና  ገድሉን ሦስት ተርጓሚያን እንደተሳተፉበት፤ በ350፣000 ብር ለመታታመም እንደበቃ  ተጠቅሷል፡፡በመጽሐፉ የሚገኘው ገቢም ሙሉ ለሙሉ ለአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ገዳም ሁለገብ ሕንፃ ግንባታ እንደሚውል ተገልጿል፡፡

 

በተጨማሪም ለገዳሙ ሁለገብ ሕንፃ ማሠሪያ ደራሲት ፀሐይ መላኩ “የንስሐ ሸንጎ” የተሰኘውን መጽሐፋቸው አበርክተዋል፡፡

 

yaba gy 5ሁለቱንም መጻሕፍት ብፁዕ አቡነ ናትናኤል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ዐቃቤ መንበር በመመረቅና በመባረክ የማኅበሩ ዋና ጸሐፊ ዲ/ን ሙሉጌታ ኃይለማርያም ተረክበዋል፡፡ ደራሲት ጸሐይ መላኩ “እመምኔት” የተሰኘው መጽሐፋቸው ለማኅበሩ ሕንፃ ግንባታ እንዲውል ከዚህ ቀደም ማበርከታቸው ይታወሳል፡፡

 

በዐውደ ጥናቱ ላይ ከተገኙት ተጋባዥ እንግዶች መካከል የቀድሞው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ባለ አደራ ከንቲባ የነበሩት አቶ ብርሃነ ደሬሳ ሲሆኑ በዚህ መርሐ ግብር ላይ በመገኘታቸው መደሰታቸውን ገልጸው መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

 

“ማኅበረ ቅዱሳን የሚመሰገንና ብዙ ቁም ነገር እየሠራ ያለ ማኅበረ ነው፡፡ አንድ ምክር ልለግሳችሁ፡፡ “ለነፍሳችሁ ብቻ ሳይሆን ለሰላምም መሥራት አለባችሁ፡፡ ሰላም ስትኖር ትረሳለች ሳትኖር ግን ታንገበግባለች፡፡ ማኅበሩ ለዚህ መቆም አለበት፡፡” ብለዋል፡፡

 

ገዳማትን አስመልክቶም ቅዱስ መጽሐፍ ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች ይላል፡፡ የተዘረጉ የኢትዮጵያውያን እጆች የታጠፈበት ጊዜ ነበር እርሱም ደርግ እግዚአብሔር የለም ብሎ ቤተ ክርስቲያን ለመዝጋት በተነሣበት በ17ቱ ዓመት የቤተ ክርስቲያን የመከራ ወራት /ዘመን/ ነበር፡፡ በዚህን ጊዜም ቢሆን ያልታጠፉ ወደ እግዚአብሔር የተዘረጉ እጆች ነበሩ፡፡ እነዚህ እጆች የመነኮሳትና የመነኮሳይያት እጆች ናቸው፤ ለዚህ ያበቃን የገዳማውያኑ ጸሎት ነው፡፡ ስለዚህ መረዳት አለባቸው” ብለዋል፡፡ ለዚህም አገልግሎት ይረዳ ዘንድ 20 ሺህ ብር ለመሥጠት ቃል ገብተዋል፡፡

 

በመርሐ ግብሩ ላይ በክብር እንግድነት ከተገኙት መካከል በኢትዮጵያ የምሥራቅ አፍሪካ ፔፕሲ ኮላ ዋና ሥራ አስኪያጅ የሆኑት አቶ ደርቤ ሥነ ጊዮርጊስ ማኅበሩ ለገዳማት ለሚያከናውነው አገልግሎት 10 ሺህ ብር ለመሥጠት ቃል የገቡ ሲሆን “የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን አጥታ አይደለም እንደዚህ የሚያስተባብርላት፣ ፕሮጀክት ቀርጾ አቅርቦ የሚፈጽም አካል ብቻ ነበር የጠፋው፡፡ እግዚአብሔር ይመስገን አሁን ማኅበረ ቅዱሳንን አስነሥቷል፡፡ የሚሠራውን ሥራ በተግባር ያየሁት በመሆኑ አብሬ እየሠራሁ ድጋፌን እቀጥላለሁ” ብለዋል፡፡

 

በመርሐ ግብሩ ማጠናቀቂያ ላይም በብፁዕ አቡነ ናትናኤል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መልካም ፈቃድ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ቃለ ምዕዳን በመስጠት መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡ በሰጡት ቃለ ምዕዳንም “አባቶቻችን የገደሟቸውን ገዳማት ለእግረኞችም ሆነ ለፈረሰኞች አይመቹም፡፡ ከዛሬ 4ዐ ዓመት በፊት ከዋልድባ ተነሥተን የኢትዮጵያ ገዳማትን ሁኔታ ለማየት ተንቀሳቅሰን ነበር፡፡ ነገር ግን አልቻልንም፡፡ ዛሬ ባለቤት ያገኘ ይመስላል፡፡ ልጆቻችን እየወጡ እየወረዱ የተዘጉትን ገዳማት በማስከፈት እየተንቀሳቀሱ ነው፡፡ እግዚአብሔር እነዚህን ልጆቻችን ስለሰጠን እናመሰግነዋለን፡፡ ….የጉርምስና ጊዜ ለመንፈሳዊ ሥራ አይመችም፡፡ ይህንን ለመሥራት ከእግዚአብሔር መመረጥ፤ መታደል ያስፈልጋል፡፡ ልጆቻችን ከኑሮ ጋር እየታገሉ ጊዜያቸውን ለማኅበራችን እንስጥ በማለት ለቤተ ክርስቲያን መሥዋእት እየሆኑ ነው፡፡ እኔም ከማኅበሩ ጎን በመቆም እታዘዛለሁ፡፡ ብለዋል፡፡

 

ብፁዕ አቡነ ሉቃስ የሰቲት ሑመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና በማኅበረ ቅዱሳን የጥናትና ምርምር ማእከል የአማካሪ ቦርድ ሰብሪሳቢ በሰጡት ቃለ ምእዳንም “ማኅበሩ ከገጠሪቱ ቤተ ክርስቲያን አንሥቶ የቤተ ክርስቲያናችን አእምሮና ልቡና እስከ ሆነው ገዳም ድረስ በመዝለቅ ከፍተኛ ሥራ እየሠሩ ነው፡፡ ገዳማት የምስጢር፣ የዜማ፤ የመጻሕፍት፤ የሊቃውንት፣ የካህናት መገኛ ናቸው፡፡ ልጆቻችን የሚሠሩት ሥራ እስከዚያ ዘልቋል፡፡ እግዚአብሔር ያስተማረው ሰው የእግዚብሔርን ሥራ ይሠራል፡፡ የእግዚአብሔርን ንብረት ይጠብቃል፡፡ ልጆቻችን ከእግዚአብሔር የተማሩት እየሠሩበት ነው፡፡ ከጎናቸው እንቁም፡፡ እኛም ከማኅበሩ ጎን ቆመን እንሠራለን፣ እንላላካለን፣ እንልካለንም፡፡” ብለዋል፡፡

 

በመጨረሻም አቡነ ናትናኤል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ዐቃቤ መንበርና የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በሰጡት ቃለምዕዳንና ቡራኬ “ያሰባችሁት ሁሉ መልካም ነገር ነውና ያሰባችሁትን ሁሉ እንድትሠሩ እግዚአብሔር ይርዳችሁ፡፡ ማኅበሩን ያስፋልን ማኅበሩን ከስም አወጣጥ ጀምሮ እኛ የሰጠነው በመሆኑ አብረን እንሠራለን ብለዋል፡፡

 

በመርሐ ግብሩ ላይ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ የገዳማት አበምኔቶችና እመምኔተች ካህናት የዩኒቨርሲቲ ምሁራንና ምእመናን ተገኝተዋል፡፡

aa center support 2005

አባቶቻችንን አንተው

aa center support 2005

menekosate 4 2

ከታላላቅ ገዳማት ለመጡ አባቶች አቀባበል ተደረገ

ታኅሣሥ 6 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

menekosate 4 2

ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርሰቲያን ታላላቅ ገዳማት ለመጡ አበምኔቶችና እመምኔቶች አቀባበል ተደረገ፡፡ በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ተልእኮ ለማሳካት የገዳማት ድርሻ በሚል በተዘጋጀው ዐውደ ጥናትና ለአምስት ቀናት በሚቆየው ሥልጠና፤ እንዲሁም በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን  ላይ ታላቅ አሻራቸውን ትተው ያለፉትን የታላቁ አባት አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ የገድል መጽሐፍ ምረቃ ላይ ለመገኘት ከሃምሳ በላይ ለሚደርሱ ገዳማት አበምኔቶችና እመምኔቶች በተደረገው ጥሪ መሠረት ከማክሰኞ ጀምሮ ርቀቱ ሳይገድባቸው አዲስ አበባ በመግባት ላይ ሰንብተዋል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳንም  ዝግጅቱን አጠናቆ በጉጉት ከመጠባበቅ አልፎ በአክብሮት እየተቀበላቸው ይገኛል፡፡

 

ዓርብ የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል አገልጋዮች በማኅበሩ ሕንፃ 6ኛ ፎቅ ላይ ለአባቶች ማረፊያ ቦታ ለማዘጋጀት በመሯሯጥ ላይ ነው የዋሉት፡፡ ፍራሽ፤ አንሶላ፤ ምንጣፍ፤ ብርድ ልብስ አሰገብተው እያነጠፉ አባቶችን እንኳን ደህና መጣችሁ በማለት በመቀበል ላይ ናቸው፡፡

 

ማኅበሩ ይህንን ሓላፊነት ለመወጣት አባቶችን በመቀበልና በማስተናገድ አሰተዋጽኦ እንዲያደርጉ ቤተ ክርስቲያንን በማገልገል ላይ ለሚገኙ መንፈሳዊ ማኅበራትና በጎ አድራጊ ምእመናን ጥሪ አድርጓል፡፡ በዚህም መሠረት ለአገልግሎቱ ከጧት ጀምሮ የደጆችሽ አይዘጉ መንፈሳዊ የአገልግሎት ማኅበር አባላት ለአባቶች የሚሆነውን ምግብ በማዘጋጀት ላይ ተጠምደዋል፡፡  አመሻሽ ላይ የማኅበሩ ዋናው ማእከል ግቢ ከ55 በላይ በሚደርሱ ገዳማት በመጡ አበምኔቶችና እመምኔቶች ደምቋል፡፡ ሁሉም የታቀደውን በጎ ዓላማ ለማሳካት በመንቀሳቀስ ላይ ነው፡፡ አባቶች ልጆቻቸውን ለመባረክ ደከመኝ ሰለቸን አላሉም፡፡ ልጆችም በረከት ለመቀበል አባቶች እግር ሥር ከመውደቅ አልሰነፉም፡፡ ፍጹም ክርስቲያናዊ መገለጫ የሆነውን ትሕትና በአባቶችም ሆነ በልጆች ዘንድ ይነበባል፡፡ በአባቶችና በመንፈስ ልጆቻቸው መካከል የሚታየው ቁርኝት ላስተዋለው ያስገርማል፡፡ በአካል ብቻ ሳይሆን በመንፈስም ክርስትና ያስተሳሰረው አንድነት፡፡

 

ምሽት 12 ሰዓት ሲሆን ደጆችሽ አይዘጉ መንፈሳዊ የአገልግሎት ማኅበር አባላት 6ኛው ፎቅ ኮሪደር መግቢያ ላይ ውሃ በባልዲና በጀሪካን ሞልተው ለበረከት ያለ እያገዛቸው 6ቱን ፎቅ ይወጣሉ ይወርዳሉ፡፡ የአባቶችን እግር ለማጠብ ሁሉም በመሽቀዳደም ላይ ቢሆንም ሁሉም ከበረከቱ ይሳተፍ ዘንድ በየተራ ለማጠብ አንድ ሰው የአንደ አባት እግር እንዲያጥብ መመሪያ ተሠጠ፡፡ ሰባት የሚደርሱ ሳፋዎች ከነውሃቸው ተቀምጠው አባቶችን ይጠባበቃሉ፡፡ አባላቱ የአባቶችን እግር ለማጠብ ተሰልፈዋል፡፡ አባቶች ከማረፊያቸው እየወጡ ልጆቻቸውን እየባረኩ በትሕትናና ፍቅር በታጀበ መስተንግዶ በልጆቻቸው እግራቸውን ታጠቡ፡፡

 

በቀጣይነት የተካሄደው ለአባቶች ማእድ ማቅረብ ሲሆን የዕለቱን ሙሉ ወጪውንና መስተንግዶውን የቻለው ደጆችሽ አይዘጉ መንፈሳዊ የአገልግሎት ማኅበር ነው፡፡ አባላቱም ለአባቶች ያዘጋጁትን ማእድ በማቅረብ ሳይሰቀቁ እንዲመገቡ በመጋበዝ ምን ይጨመር? እያሉ ይጠይቃሉ፤ ወጥ ያወጣሉ እንጀራ ይጨምራሉ፡፡ አባቶች ትሕትናን እንደተላበሱ ለኛ ይህ አይገባም የሚሉ ይመስላሉ፡፡ ደስታ ግን ይነበብባቸዋል፡፡

 

menekosate 2 2ማእዱን እንደተመገቡ  የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ ቀሲስ ዶክተር ሰሙ ምትኩ የእንኳን ደህና መጣችሁ መልእክት ለማስተላለፍ ቅድሚያውን ወሰዱ፡፡ “የቤተ ክርስቲያን መሠረቷ ገዳማት ናቸው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ጠነከረች የሚባለውም የገዳማት ጥንካሬ የሚያመጣው ነውና በዚህ ሁኔታ ላይ እንድንወያይ፤ ነገ ምን ማድረግ እንደሚገባን እንድንነጋገር፤ እኛም የምናስበውን ለማሳየት እንድንችል እንድትመክሩን፤ እንድተጸልዩልን ነው የተሰባሰብነው፡፡ እናንተን ለማየት በመታደላችን እጅግ ደስተኞች ነን፡፡ ቀሪውን ጊዜም መልካም ነገር የምናቅድበትና የምንፈጽምበት እንዲሆን እንመኛለን” ያሉ ሲሆን ደጆችሽ አይዘጉ መንፈሳዊ የአገልግሎት ማኅበር ላከናወነው አርአያነት ያለው ተግባር ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

 

የደጆችሽ አይዘጉ መንፈሳዊ የአገልግሎት ማኅበር ተወካይ አቶ ሙሉጌታ በመርሐ ግብሩ ላይ የተሰማቸውን እንዲገልጹ እድሉ የተሰጣቸው ሲሆን “እግዚአብሔር ዛሬ ታላቅ ነገር አድርጎልናል፡፡ በረከት ለማግኘት ከከተማ ወደ ገጠር ነበር የምንወጣው፡፡ እግዚአብሔር የማይታሰብ ነገር አደረገልን፡፡ ሰው እንጨት ሊቆርጥ ወደ ተራራ ይወጣል እንጂ ተራራው ከነ እንጨቱ ወደ ሰው አይመጣም፡፡ እግዚአብሔር የሚሳነው ነገር ስለሌለ ዛሬ አባቶቻችንን ከነበረከታቸው ወደ እኛ አመጣቸው፡፡ አባቶቻችን እናንተ ባትኖሩ እኛም አንኖርም፡፡ እግዚአብሔር እናንተን ስለሰጠን ደስተኞች ነን” ብለዋል፡፡

 

በመጨረሻም አባቶች ከገዳም ወጥተው አዲስ አካባቢ ላይ የሚገኙ  በመሆናቸው ምግቡም ሆነ ውኃው በመለወጡ ምክንያት ሥጋዊ ሕመምmenekosate 2 1 ቢሰማቸው የማኅበሩ አባላት የሆኑ የሕክምና ዶክተሮችና ነርሶች 24 ሰዓት እነሱን ለማገልገል መመደባቸው ተገለጸላቸው፡፡ እንዲሁም ማንኛውንም አገልግሎት ቢፈልጉ እነሱን ለማገልገል የተመደቡ ወንድሞችና እኅቶች ስለሚገኙ የሚሹትን ነገር ሳይሰቀቁ እንዲጠይቁ በማሳሰብ የምሽቱ መርሐ ግብር በአባቶች ቡራኬ ተጠናቋል፡፡

 

ይቆየን……….

mahbre posterpsd

“ለቤተ ክርስቲያን ተልዕኮ መሳካት የገዳማት ድርሻ” በሚል ዐውደ ጥናት ይካሄዳል

ታኅሣሥ 4 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

  • የአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ የገድል መጽሐፍ ይመረቃል

mahbre posterpsdየኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ተልእኮ ለማሳካት የገዳማት ድርሻ በሚል መሪ ቃል የተዘጋጀ አውደ ጥናት ታህሣሥ 6 ቀን 2005 ዓ.ም. ከቀኑ 7፡00 ሠዓት ጀምሮ 6 ኪሎ በሚገኘው በኢትዮጵያ ስብሰባ ማእከል ከሃምሳ በላይ የሚደርሱ ከታላላቅ ገዳማት የተውጣጡ አበምኔቶች በተገኙበት እንደሚካሄድ በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ዳይሬክተር ዲያቆን አእምሮ ይሔይስ ገለጹ፡፡

 

በዕለቱም ከዐውደ ጥናቱ ጋር ተያይዞ በገዳማት ላይ ጎልተው የሚታዩትን  ችግሮች መቅረፍ ይቻል ዘንድ ማኅበረ ቅዱሳን 12 ፕሮጀክቶችን በመቅረጽ በገዳማት ላይ ተግባራዊ ለማድረግ የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር አዘጋጅቷል፡፡ በዚህም መሠረት ከ5000 ለሚደርሱ ምእመናን ጥሪ የተደረገ ሲሆን ዋነኛ ዓላማውም ለፕሮጀክቶቹ ማስፈጸሚያ የሚውል ገቢ ለማሰባሰብ መሆኑን ከቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡

 

በተጨማሪም በዚሁ ዕለት የታላቁ አባት የአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫና የአባ በጸሎተ ሚካኤል የገድል መጽሐፍ የሚመረቅ ሲሆን ተተርጉሞ ለኅትመት ለማብቃት ከሦስት ዓመት በላይ እንደፈጀ ተገልጿል፡፡

 

በመርሐ ግብሩ ላይ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በአገልግሎት ላይ የሚገኙ መንፈሳዊ ማኅበራትና ምእመናን እንደሚገኙ ይጠበቃል፡፡

 

በተያያዘ  ዜና ከየገዳማቱ ለተውጣጡት ከሃምሳ በላይ አበምኔቶች የሚሳተፉበትና ከታኅሣሥ 7 -11 ቀን 2005 ዓ.ም. የሚቆይ ሥልጠና መዘጋጀቱን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ዳይሬክተር ዲያቆን አእምሮ ይሔይስ ገልጸዋል፡፡  ሥልጠናው የሚያተኩርባቸው ርዕሰ ጉዳዮችን ሲያብራሩም “ገዳማት በውስጣቸው ያለውን ሀብት እንዴት መጠቀም ይችላሉ? በገዳማት ውስጥ የሥራ ፈጠራን እንዴት ማዳበር ይቻላል? እንዴትስ ውጤታማ ሥራ መሥራት ይቻላል? ከአካባቢ ጥበቃ ጋር በተያያዘ ገዳማት ያላቸውን የደን ሀብት እንዴት ተንከባክበው መያዝና መጠቀም ይችላሉ?  በቅርስ አያያዝ በኩልም በፈራረሰ ዕቃ ቤት ውስጥና አመቺ ባልሆነ ሁኔታ ላይ የሚገኙትን ቅርሶች በተሻለና በተቀናጀ መንገድ ጠብቀው  ለተተኪው ትውልድ እንዴት ማስተላለፍ ይችላሉ? የሚሉት ላይ ያተኩራል” ብለዋል፡፡

 

ሥልጠናው በአዲስ አበባ ዩኒቨርሰቲ ምሁራን፤ በቅርስ ጥበቃ ባለሙያዎችና በተጋባዥ ምሁራን አማካይነት  እንደሚሰጥ ዲያቆን አእምሮ ይሔይስ ጨምረው ገልጸዋል፡፡

debube omo 2 1

በደቡብ ኦሞ ከሰባት መቶ በላይ ሰዎች ተጠመቁ

ታኅሣሥ 1 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ


debube omo 2 1በማኅበረ ቅዱሳን የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ ፕሮግራም አስተባበሪነት፤ በደቡብ ኦሞ ሀገረ ስብከት ሥር የሚገኙና በልዩ ልዩ ቤተ እምነቶች ውስጥ የነበሩ ከሰባት መቶ በላይ ኢትዮጵያውያን ሥርዓተ ጥምቀት ተፈጽሞላቸው ወደ እናት ቤተ ክርስቲያን ተመለሱ፡፡ በሜጸር የቅዱስ ሚካኤል እንዲሁም በቶልታ የቅድስት ሥላሴ አብያተ ክርስቲያናት ውስጥ ኅዳር 23 ቀን 2005 ዓ.ም. በተከናወነው ሥርዓተ ጥምቀት ሀብተ ወልድና ስመ ክርስትና ያገኙ ሰዎች በማኅበረ ቅዱሳን የጂንካ ማእከልና በሰንበት ትምህርት ቤት ጥምረት በሁለት ልዩ ልዩ የስብከት ኬላዎች አማካኝነት ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ሲማሩ የቆዩ ናቸው፡፡

 

debube omo 2 2አዳዲስ ተጠማቂያኑ ለዝግጅት ክፍላችን በሰጡት አተያየት ፡ በተፈጸመላቸው ሥርዓት ጥምቀት እጅግ በጣም መደሰታቸውን ገልጸው፤ በአቅራቢያቸው ቤተ ክርስቲያን እንዲታነፅላቸው ጥያቄ አቅርበዋል፡፡ በጉዳዩ ላይ ያነጋገርናቸው ብፁዕ አቡነ ኤልያስ የደቡብ ኦሞ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል  “የምእመናኑ ጥያቄ ተገቢ ነው፡፡ አብያተ ክርስቲያናቱ ሲቋቋሙ አብሮ መተዳደሪቸውም ሊታሰብ ይገባዋል፤ በአንዳንድ ቦታዎች ላይ እንዳስተዋልነው ምእመናን በቅንነት በዚህ ቦታ እንዲህ ያለ ታቦት ይተከልልን እኛ ሙሉ ወጪውን እንሸፍናለን በማለት ያሳነፅዋቸው አብያተ ክርስቲያናት ምእመናኑ በሕይወት እስካሉ ድረስ ያገለግሏቸውና፤ እነሱ ከዚህ ዓለም በሞተ ሥጋ ሲለዩ አገልግሎቱ እየተቋረጠ አብያተ ክርስቲያናቱ እስከ መዘጋት የደረሱባቸው ሁኔታዎች አሉ፡፡ ስለሆነም ቤተ ክርስቲያኗ እንዴት ትገለገላለች? በሚለው ላይ ማኅበረ ቅዱሳንን ጨምሮ በመላው ዓለም የሚገኙ የቤተ ክርስቲኒቱ ልጆች ሊያስቡበት ይገባል፡፡ አብያተ ክርስቲያናትም ሁል ጊዜ በልመና መተዳደር የለባቸውም” ብለዋል፡፡

 

በማኅበረ ቅዱሳን ስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ ፕሮግራም፤ የፕሮግራሙ አስተባባሪ የሆኑት ሊቀ ብርሃናት ሃይማኖት ተስፋዬ ስለ ተከናወነው አገልግሎት ሲናገሩ “ስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ ፕሮግራሙ በዐስር ዓመታት ለመፈጸም ከያዛቸው ዕቅዶች አንዱ በጂንካ ማእከል አማካኝነት ለንዑሳን ክርስቲያኖች በአቅራቢያቸው የስብከት ኬላዎችን (ቃለ እግዚአብሔር የሚሰሙባቸው ቤቶች)  እንዲቋቋምላቸውና መሠረታዊ የሃማኖት ትምህርት እንዲያገኙ ማድረግ ነበር፡፡ ይህም በእግዚአብሔር ቸርነት የተፈጸመ ነው፡፡ በቅርቡም በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል መተከል ሀገረ ስብከት በማንዲራና ድብጤ ወረዳዎች ሲያስተምራቸው ለነበሩት ሰዎች በቅርቡ የማጥመቅ ተግባርን ለመፈጸም ዝግጅቱ ተጠናቋል” ብለዋል፡፡

 

debube omo 2 4የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያው በቶልታና ሜጠር ቀበሌዎች ላስጠመቃቸው አዳዲስ ምእመናን በቀጣይ ለሚፈጽምላቸው  እገዛ አስመልክተው ሊቀ ብርሃናት ሃማኖት ተስፋዬ እንዲህ ብለዋል፡፡ “የልጅነት ጥምቀት አግኝተው በቅርቡ ወደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ለገቡ ምእመናን በአቅራቢያቸው ሥርዓተ አምልኮ የሚፈጽሙባቸውን አብያተ ክርስቲያናትን ማነፅና እነሱንም ማጽናት ይጠበቅብናል፡፡”

eresha be 3

የበኬ ደብረ ምሕረት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን የልማት ሥራ ተጎበኘ

ታኅሣሥ 1 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

 

eresha be 3በማኅበረ ቅዱሳን የአዲስ አበባ ማዕከል ሥራ አሥፈጻሚ አባላትን ያቀፈ የልዑካን ቡድን በበኬ ደብረ ምሕረት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን እየተከናወነ የሚገኘውን የልማት ሥራ ለመመልከትና ከደብሩ አስተዳደር አካላት ጋር ለመወያየት ኅዳር 23 ቀን 2005 ዓ.ም. ጉብኝት አካሄደ፡፡

 

የአዲስ አበባ ማእከል ከበኬ ደብረ ምሕረት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን አስተዳደርና ሰበካ ጉባኤ ጋር ባደረገው የውል ሥምምነትeresha be 2 መሠረት በባለሙያ አስጠንቶ ዘመናዊ የግብርና ኤክስቴንሽን መርሐ ግብሮች ተግባራዊ ለማድረግ ጥረት ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ በተያዘው እቅድ መሠረት እሰካሁን ከተከናወኑት ውስጥ ደግሞ የቤተ ክርስቲያኑ ይዞታ በሆነው 3 ሄክታር መሬት ላይ የተዘራው የጤፍ እርሻ የሚገኝበትን መቃኘት የመጀመሪያው የጉብኝቱ አካል ነበር፡፡

 

የጤፉ እርሻ ለዓይን ይማርካል፡፡ ከ250 አስከ 300 ካሬ ሜትር የሚሆነው ከሌላው ማሳ ለየት ባለ ሁኔታ በቁመትም፤ ሆነ በያዘው የፍሬ መጠን ከፍተኛነት ይለያል፡፡ ለአጨዳ የደረሰ በሚመስል መልኩ ወደ ቢጫነት አዘንብሏል፡፡ ቀሪውም ባማረ ሁኔታ ጎልቶ ይታያል፡፡ ከፍተኛ ክትትል እንደተደረገበትም ያመለክታል፡፡

 

የቤተ ክርስቲያኑ አስተዳዳሪ የሆኑት አባ ገብረ አማኑኤል ቦታው ጠፍ የነበረና የከብቶች መዋያ ሆኖ መቆየቱንና ይህንንም ችግር ለመቅረፍ ከማኅበረ ቅዱሳን አዲስ አበባ ማዕከል ጋር በተደረገው ስምምነት መሠረት በባለሙያ ተጠንቶና ታርሶ ፍሬ ለማየት እንደበቁ የገለጹ ሲሆን ወደፊትም ተደጋግፎ የተሻለ ሥራ ለመሥራት እንደተዘጋጁ በጉብኝቱ ላይ ተናግረዋል፡፡

 

“በእርሻ ሥራው ላይ የደብሩ ካህናት የንስሐ ልጆቻቸውን በማስተባበር፤ ለዘር የሚሆን ጤፍ በማቅረብ፤ በጉልጓሎና ዘር በሚዘራበት ውቅት ቤተሰቦቻቸውን ጭምር በማሰማራት፤ ቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ በመማር ላይ የሚገኙ ከ200 በላይ የአብነት ተማሪዎች፤ የደብሩ አስተዳደር፤ ካህናትና ዲያቆናት ተሳትፈውበታል፡፡ ምርቱም በመማር ላይ ለሚገኙት የአብነት ተማሪዎች የምግብ ፍጆታነት ይውላል” በማለት የገለጹት ደግሞ የቀድሞው የቤተ ክርስቲያኗ ሰበካ ጉባኤ ምክትል ሰብሳቢ የሆኑት አቶ ከፍያለው አየለ ናቸው፡፡

 

eresha be“የግብርና ኤክስቴንሽን መርሐ ግብሮችን ለመጠቀም ጥረት አድርገናል፡፡ ለማስተማር የፈለግነው የአካባቢው አርሶ አደሮችና ምእመናን ከቤተ ክርስቲያን በጎ ተሞክሮዎችን እንዲወስዱ ለማድረግ ነው፡፡ በበሬ ብቻ ሳይሆን በትራክተር እንዲታረስም አድርገናል፡፡ ከ3 ሄክታር መሬቱ ላይ ከ250 እሰከ 300 ካሬ ሜትሩ ለሙከራ ምርጥ ዘር ተጠቅመናል፡፡ የትኛው የተሻለ እንደሆነ ለሁሉም ለማሳየት የቻልንበት ነው፡፡ ገና ሳይታጨድ ልዩነቱም ጎልቶ ይታያል፡፡ በሚቀጥለው አመትም ጤፍ በመሥመር መዝራትን ተግባራዊ የምናደርግበት ሁኔታ እናመቻቻለን፡፡ ይህንን የምናደርገው ምእመናን የቤተ ክርስቲያናችንን ተሞክሮ ተመልክተው እነሱም እንዲጠቀሙበት ለማስተማር ነው፡፡” በማለት ወይዘሪት መቅደስ አለሙ በአዲስ አበባ ማእከል የማኅበራዊ አገልግሎትና ልማት ክፍል ሰብሳቢ በጉብኝቱ ላይ ገልጸዋል፡፡

 

በቀጣይነት የተካሄደው አብነት ትምህርት ቤቱ የሚገኝበት ሁኔታ ለመቃኘት የተደረገ ጉብኝት ነው፡፡ የአብነት ትምህርት ቤቱ በ3 መምህራን ከ200 በላይ ተማሪዎችን በማቀፍ የአቋቋም፤ የቅኔ፤ እንዲሁም የቅዳሴ ትምህርቶች የሚሰጥበት ተቋም ነው፡፡

 

በሁለት አዳራሾች ውስጥ መኝታቸውን ያደረጉት የአብነት ተማሪዎቹ የመኝታቸው ጉዳይ እጅግ አሳሳቢ ነው፤ አልጋቸው በርብራብ እንጨትeresha be 4 የተዘጋጁ ናቸው፤ የሳር ፍራሽና ካርቱን አንጥፈውበታል፡፡ አንዱን ከአንዱ ለመለየት በማዳበሪያ ተከፋፍሏል፤ በአንዱ አዳራሽ ውስጥ አዳራቸውን የሚያደርጉት ተማሪዎች ብዛት ከአንድ መቶ ይበልጣል፡፡ አዳራሹ ውስጥ እሳት ቢነሣ ወይም በሽታ ቢገባ የሚተርፍ ያለ አይመስልም፡፡ አንድ የማብሰያ ክፍል ሲኖር ሁሉንም ማስተናገድ ስለማይችል የተወሰኑት ተማሪዎች ውጪ ሜዳው ላይ ምግባቸውን ለማብሰል ይገደዳሉ፡፡

 

የቤተ ክተርስቲያኑ አስተዳደር ጉባኤ ያለውን ችግር በመረዳት ለሰንዳፋ በኬ የማኅበረ ቅዱሳን ማእከል፤ በቅደም ተከተልም ለአዲስ አበባና ለዋናው ማእከል የችግሩ አሳሳቢነት በማሳወቅ ጥናት ተደርጓል፡፡ በጥናቱ መሠረት የአብነት ትምህርት ቤቱን ለማደራጀትና ለማጠናከር ፤ ተማሪዎቹም ተምረው የነገዎቹ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እንዲሆኑ ለማስልቻል ጥረት በመደረግ ላይ  ይገኛል፡፡ በማኅበረ ቅዱሳን የአዲስ አበባ ማእከል ከፍተኛ በጀት በመመደብ የአብነት ትምህርት ቤቱን ዘመናዊ ሕንፃ ለመገንባት ዝግጅት በማድረግ ላይ እንደሚገኝና ግንባታውንም በዚህ ዓመት ይጀመራል ተብሎ እንደሚጠበቅ በጉብኝቱ ላይ ተገልጧል፡፡

 

በመጨረሻም በጋራ ውይይት የተካሄደ ሲሆን በቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ሥራዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ የሁሉም ድጋፍ እንደሚያስፈልግ የቤተ ክርስቲያኑ አስተዳዳሪ አባ ገብረ አማኑኤል ጥሪያቸውን ያስተላለፉ ሲሆን በልማት ሥራው ላይ ለተሣተፉ ሁሉ ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡ በጉብኝቱ ላይ የሰንዳፋ ወረዳ ቤተ ክህነት ሓላፊዎች፤ የደብሩ አስተዳደር፤ ካህናትና ዲያቆናት፤ የደብሩ የሰበካ ጉባኤ አባላት፤ የማኅበረ ቅዱሳን የሰንዳፋ ማእከል ሓላፊዎችና አባላት፤ ጥሪ የተደረገላቸው የአጥቢያው ምእመናን ተገኝተዋል፡፡

 

በኬ ደብረ ምሕረት ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን በዳግማዊ ዐፄ ምኒልክ ዘመነ መንግሥት በ1860ዎቹ ውስጥ እንደ ተተከለ ይነገራል፡፡

mkmesfin1

የማዕረግ ተመራቂው የወርቅ ሜዳልያውን ለማኅበሩ አበረከተ

29/03/2005ዓ.ም

በእንዳለ ደምስስ

ደብረ ዘይት በሚገኘው በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ እንስሳት ህክምናና ግብርና ኮሌጅ በ2004 ዓ.ም. የተመረቀው ዶክተር መስፍን ማሞ በአጠቃላይ ውጤት (GPA) 3.98  እጅግ በጣም ከፍተኛ ማዕረግ በማምጣት ተመርቋል፡፡ ኮሌጁም ላስመዘገበው ውጤት Outstanding Student Of The Year 2012 College Of Veternary & Agriculture በማለት ኮሌጁ በበላይነት ላጠናቀቁ ተማሪዎች የሚሰጠውን የወርቅ ሜዳልያ ሽልማት አበርክቶለታል፡፡

mkmesfin1

ዶክተር መስፍን ማሞ ይህንን ሽልማት በመያዝ ወደ ማኅበረ ቅዱሳን ዋናው ማዕከል በመምጣት “በትምህርቴ ባስመዘገብኩት ውጤት ያገኘሁት ሽልማት ነው፡፡ ለኔ አይገባኝም፡፡” በማለት ለማኅበሩ እንደሚሰጥ አሳወቀ፡፡

 

በርክክቡ ላይ ከኮሌጁ የተሸለመውን  የወርቅ ሜዳልያ ለማኅበረ ቅዱሳን  ለምን መሥጠት እንደፈለገ ዶክተር መስፍን ማሞ ሲገልጽ “ማኅበሩ በቤተ ክርስቲያናችን ዙሪያ በሀገር ውስጥም ሆነ በመላው ዓለም ከፍተኛ አገልግሎት እያበረከተ ይገኛል፡፡ ቤተ ክርስቲያንን በማስተዋወቅና ምዕመናንን በማስተማር እያበረከተ ላለው ጥረት ከፍተኛ አክብሮት አለኝ፡፡ በግቢ ጉባኤ አማካይነት በሥነ ምግባር የታነጸና የዓላማ ሠው እንድሆን ማኅበሩ ከፍተኛ እገዛ አድርጎልኛልና ያለኝን ታላቅ አክብሮት ለመግለጽ ስል ይህንን ከኮሌጁ የተሸለምኩትን የወርቅ ሜዳልያ ሰጥቻለሁ” ብሏል፡፡

mkmesfin2የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጸሐፊ ዲያቆን ሙሉጌታ ኃይለ ማርያም የወርቅ ሜዳልያውን በተረከቡበት ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት  “የማኅበረ ቅዱሳን አባላት በግቢ ጉባኤያት ቆይታቸው በትምህርታቸው ከፍተኛ ውጤት በማስመዝገብ የተሸለሙትን ሜዳልያ ለማኅበሩ ሲያበረክቱ ይህ ለሁለተኛ ጊዜ ነው፡፡

 

ተማሪዎች የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት ከመደበኛው ትምህርታቸው ውጪ ጊዜያቸውን በፕሮግራምና  በአግባቡ መጠቀም ከቻሉ ለውጤት መብቃት እንደሚችሉ መልዕክት የሚያስተላልፍ ነው፡፡ ሽልማቱ ለማኅበራችን እንዲሁም ለቤተ ክርስቲናችን ታላቅ ኩራት ነው፡፡” በማለት የገለጹ ሲሆን ዶክተር መስፍን ማሞ ላደረጉት አርአያነት ያለው ተግባር ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

 

ከዚህ ቀደም ከጅማ ጤና ሳይንስ ኮሌጅ በከፍተኛ ማዕረግ የተመረቁት ዲያቆን ዶክተር እንግዳ አበበ የተሸለሙትን የወርቅ ሜዳልያ ለማኅበረ ቅዱሳን በሥጦታ እንዳበረከቱ ይታወቃል፡፡

nebabe 2 1

የንባብ ባሕልን ለማሳደግ ውይይት ተካሄደ

ኅዳር 26 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ


የንባብ ባሕልን በማሳደግ በመረጃና በእውቀት የበለጸገ ማኅበረሰብ እንፍጠር በሚል ርዕስ የማኅበረ ቅዱሳን የጥናትና ምርምር ማእከልnebabe 2 1 ያዘጋጀው የውይይት መድረክ  ኅዳር 22 ቀን 2005 ዓ.ም. ከቀኑ 8፡00 ስዓት ላይ በማኅበሩ ሕንፃ ላይ ተካሄደ፡፡

 

ቀሲስ ዶ/ር ሰሙ ምትኩ የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ በመርሐ ግብሩ ላይ ለተገኙት እንግዶች የእንኳን ደህና መጣችሁ መልእክት ያስተላለፉ ሲሆን የውይይት መድረኩ የተዘጋጀበትን ዋነኛ ምክንያት ሲገልጹም “በሀገራችን ብሎም በቤተ ክርስቲያናችን በጣም በአሳሳቢ ሁኔታ እየቀነሰ የመጣውን የንባብ ባሕል ለማሳደግ እንዲቻል የተዘጋጀ የውይይት መድረክ ነው፡፡ የማያነብ ትውልድ አዲስ ነገር መፍጠር አይችልም፤ አዲስ ነገርንም ለመቀበል ያስቸግረዋል፡፡ የንባብ ባሕላችን ምን ላይ እንደሚገኝ፤ ያጋጠሙ ችግሮችና ሊወሰዱ የሚገባቸው መፍትሔዎች ላይ ለመወያትና እንዲሁም ቤተ ክርስቲያን ትውልዱን በእውቀትና በመረጃ ከማነፅና ከመቅረፅ አንጻር ሊኖራት የሚገባት ሚና ምን መሆን እንዳለበት ለማመላከት ነው፡፡” ብለዋል፡፡

 

nebabe 3የውይይት መድረኩ በአቶ ወንድወሰን አዳነ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የኢትዮጵያ ቋንቋዎች ሥነ ጽሑፍ ትምህርት ክፍል መምህር የተመራ ሲሆን ዲያቆን ያረጋል አበጋዝ ለውይይት መድረኩ መነሻ የሚሆን ጥናታዊ ጽሑፋቸውን አቅርበዋል፡፡ ባቀረቡት ጽሑፍም “ሥነ ፍጥረት የሚነበብ መጽሐፍ ነው፡፡ መጽሐፍ እግዚአብሔር በመጀመሪያ ለፍጥረቱ የሰጠው ትልቁ ሥጦታ  ነው፡፡” በማለት የጥናት ጽሑፋቸውን በመጀመር በመጽሐፍ ቅዱስ ስለ መጻሕፍት የተነገሩትን ጠቅሰዋል፡፡ ከእነዚህም መካከል” በእግዚአብሔር ቃል ሰማዮች ፀኑ፤ ሠራዊታቸውም ሁሉ በአፉ እስትንፋስ የባሕርን ውኃ እንደ ረዋት የሚሰበስብ ቀላዮችንም በመዝገቦች የሚያኖራቸው” መዝ.86፤6 “በእግዚአብሔር መጽሐፍ ፈልጉ አንብቡም አፌ አዟልና” (ኢሳይያስ 34፤16) በማለት ጠቅሰዋል፡፡ በተጨማሪም ከቅዱሳን አበው መካከል “ቅዱሳት መጻሕፍትን አለማወቅ የስህተት ሁሉ ምንጭ ነው” በማለት ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ከተናገረው በመነሣት የቅዱሳት መጻሕፍት ጠቀሜታን  አብራርተዋል፡፡

 

መጻሕፍትን የማንበብ ፋይዳን አስመልክቶም ተጠቃሽ ናቸው ያሏቸውን ነጥቦች አንሥተዋል፡፡ ከእነዚህም መካከል፤ መጻሕፍት በዘመናት ሂደት የተከማቹ የሰው ልጆች የእውቀት መዛግብት የሚተላለፍባቸው መንገዶች መሆናቸው፤ መጻሕፍት ጓደኛ ስለመሆናቸው፤ መጻሕፍት የመንፈስ ምግቦች መሆናቸው፤ መጻሕፍት አንድን ርዕሰ ጉዳይ ወጥና ምሉዕ በሆነ ሁኔታ ለመዳሰስ ያስችላሉ፤ መጻሕፍት ተጠቃሽ /Quatable/ ናቸው፤ መጻሕፍት በተሳሳተ መንገድ መጥቀስም መጠቀስም ባያስቀሩም ስህተቶችን ይቀንሳሉ፤ መጻሕፍት ትውልድን ይሻገራሉ በማለት የመጻሕፍትን ፋይዳ በዝርዝር ዳስሰዋል፡፡

 

ዲያቆን ያረጋል አበጋዝ የንባብ ልምድ በኢትዮጵያ አስመልክቶ ባቀረቡት ትንተናም በዚህ ርዕሰ ጉዳይ ላይ ጥናቶች በጥልቀት ያለመሠራታቸውና አንድ ጥናት አቶ አለም እሸቱ የተባሉ ተመራማሪ  ሙከራ ማድረጋቸውን ገልጸዋል፡፡ በጥናታቸውም መሠረት በ220 ሰዎች ላይ ለናሙና ያህል በቀረበ መጠይቅ ለምን መጻሕፍትን እንደማያነቡ በሰጡት ምላሽ “ላይኔ ስለምፈራ አላነብም፤ ሳነብ አይገባኝም፤ ምክንያቱን አላውቅም፤ የአውሮፓ እግር ኳስ እያለ እንዴት አነባለሁ፤ ትላልቅ መጻሕፍትን ሳይ ተስፋ ያስቆርጡኛል፤ ከቤተሰብ አልለመድኩም፤ ሴት ልጅ ቤት ውሰጥ ቁጭ ብላ ቤተሰብን ማገዝ እንጂ ለማንበብ አይፈቀድላትም ፤. . . የሚሉ ምላሾችን መስጠታቸው ንባብ በኢትዮጵያ ውስጥ አለማደጉን የሚያመላክቱ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡

 

በጥናታቸው ማጠቃለያም የንባብ ባሕልን ለማሳደግ መፍትሔ ይሆናሉ ያሏቸውንም ጠቁመዋል፡፡ የንባብ ፍላጎት እንዲኖር ማድረግ፤ ከሕፃንነት ጀምሮ የማንበብ ፍቅርና ልምድ እንዲኖር ማድረግ፤ የመጻሕፍት ስብስብና ክምችት መፍጠር እንደ መፍትሔ ካቀረቧቸው ውስጥ ይጠቀሳሉ፡፡

 

nebabe 2 2ጥናቱ ከቀረበ በኋላም በንባብ ባሕል ላይ ያተኮረ ውይይት የተካሄደ ሲሆን ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ የዩኒቨርስቲ ምሁራንና ተማሪዎች እንዲሁም ተሳታፊዎች አስተያየቶቻቸውንና የመፍትሔ አሳቦቻቸውን አቅርበዋል፡፡ በአብዛኛው ከተጠቀሱት ውስጥም የንባብ ባሕላችንን ለማሳደግ በዋነኛነት ቤተሰብና ትምህርት ቤቶች ከፍተኛ ሓላፊነት እንዳለባቸው ፤ ልጆች ከሕፃንነት ጀምሮ ንባብን ባሕል አድርገው እንዲያድጉ ከፍተኛ ሥራ መሠራት እንደሚገባው አመላክተዋል፡፡

 

በመጨረሻም ማኅበረ ቅዱሳን አንባቢ ትውልድን ለመፍጥር በሚያደርገው አገልግሎት ውስጥ መጻሕፍትን የማሰባሰብ፤ ቤተ መጻሕፍቱን በዘመናዊ መልክ የማደራጀት ሥራ በመሥራት ላይ እንደሚገኝና  በአሁኑ ወቅት ቤተ መጻሕፍቱ ከሁለት ሺህ የማይበልጡ መጻሕፍትን ብቻ አሰባስቦ አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን፤ በዐራት ዓመታት ውስጥም የመጻሕፍቱን ቁጥር ሃምሳ ሺህ ለማድረስ መታቀዱን የጥናትና ምርምር ማእከሉ ዋና ዳይሬክተር ዲያቆን ዮሐንስ አድገ የገለጹ ሲሆን ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ ምሁራንና ምእመናን አንባቢ ትውልድን ለመፍጠር በሚደረገው ጥረት ውስጥ እገዛ እንዲያደርጉ ጥሪያቸውን አቅርበዋል፡፡

 

በውይይቱ ላይ ጥሪ የተደረገላቸው ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ የዩኒቨርሲቲ ምሁራንና ተመራማሪዎች፤ እንዲሁም ተማሪዎችና ምእመናን ተገኝተዋል፡፡