ዐሥራ አምስተኛው ዙር ሐዋርያዊ የጉዞ መርሐ ግብር በተሳካ ሁኔታ ተጠናቀቀ፡፡

በደረጀ ትዕዛዙ
ማኅበረ ቅዱሳን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን ትክክለኛ አስተ ምህሮ ለምእመናን ለማዳረስ ከሚጠቀምባቸው መርሐ ግብሮች አንዱ የሆነውና በደቡብ ኢትዮ ጵያ ቦረና ጉጂ ሊበን ዞኖች ሃገረ ስብከት የተካሔደው  የአሥራ አምስተኛው ዙር ሐዋርያዊ ጉዞ በተሳካ ሁኔታ ተጠናቀቀ፡፡ እንዲህ ያለ መርሐ ግብር በተከታታይ ሊካሔድ እንደሚገባ የአካባቢው ምእመናን ቿይቀዋል፡፡
በማኅበሩ ትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል አዘጋጅነት ከየካቲት 11- 20 2003 ዓ.ም ድረስ የተካሔደው ይኸው መርሐ ግብር ቦረና ጉጂ ሊበን ዞኖች ሀገረ ስብከት የሚገኙ አምስት ከተሞችን የሸፈነ መሆኑን የመርሐ ግብሩ አስተባባሪ ዲ/ን ምትኩ አበራ ተናግረዋል፡፡

አራት መምህራንና አሥራ ሰባት ዘማሪያንን እንዲሁም ሌሎች አባላትን ያካተተው ይኸው የልኡካን ቡድን ይዞት ከተነሣው ተልእኮ አንጻር የተሻለ አገልግሎት ሰጥቶ መመለሱን የገለጡት አስተባባሪው በዚህም ምእመናኑ እጅግ ተደስተዋል ብለዋል፡፡

በሐዋርያዊ ጉዞው ትክክለኛውን የቤተክ ርስቲያን ትምህርት እና ዝማሬ ወደ ምእመናኑ ማድረስ ዋና ዓላማው አድርጎ የተንቀሳቀሰው ይኸው የልኡካን ቡድን፤ በሀገረ ስብከቱ በሚገኙ ክብረ መንግሥት፣ ሻኪሶ፣ ዋደራ፣ ቦሬ እና ነገሌ ቦረና ከተሞች በሚገኙ አምስት አብያተ ክርስቲያናት እንዲሁም በምእምናን ጥያቄ መሠረት ከዕቅድ በላይ በሁለት አጥቢያ አብያተ ክርስቲያንም አገልግሎቱን ሰጥቷል ብለዋል፡፡ በዚህም የሐዋርያዊ ጉዞው ቡድን ከሕዝቡ ተቀባይነትን፣ ከበሬታንና ፍቅርን አግኝቶ መመለሱን አስረድተዋል፡፡

ትምህርተ ወንጌሉ በአማርኛና በኦሮምኛ ቋንቋዎች መሰጠቱ ምእመናን ቃለ እግዚአብሔርን በአግባቡ እንዲረዱ ያስቻለ ከመሆኑም በተጨማሪ የልኡካን ቡድኑ አባላት የሆኑ ካህናት በቅዳሴ እና በዓመታዊ ክብረ በዓል ወቅት የቤተ መቅደስ አገልግሎት መስጠታቸው አገልግሎቱን ይበልጥ የተሳካ እንዲሆን አግዟል ብለዋል፡፡

የልኡካን ቡድኑ ከቤተክርስቲያኒቱ የስብከተ ወንጌል ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ ፈቃድ ይዞ በሕጋዊነት ተንቀሳቅሷል፡፡ ሆኖም በአንዳንድ ከተሞች በዓላማቸው የተሐድሶ እንቅ ስቃሴውን ለማራመድ በሚጥሩ ግለሰቦች መርሐ ግብሩን የማደናቀፍ አዝማሚያ አጋጥሞት አንደነበር ዲያቆን ምትኩ አበራ ተናግረዋል፡፡ ይሁንና በቤተክርስቲያኒቷ ሥርዓትና መመሪያ መሠረት የሚካሔድ ሕጋዊ አገልግሎት ስለሆነ የፈቃድ ወረቀቱን ለሕጋዊ አካላት በማሳየት እና ከየደብሩ ሓላፊዎች እና ከምእመናኑ ጋር በመነጋገር መርሐ ግብሩ ሳይስተጓጎል ከተጠበቀው በላይ የተሳካ ሆኖ መጠናቀቁን አብራርተዋል፡፡

መርሐ ግብሩ በተካሔደባቸው አካባቢዎች ከቤተክርስቲያን ሥርዓትና መመሪያ ውጪ የሚንቀሳቀሱ ሰባክያንና ዘማሪያን ስፍራውን ደጋግመው በመጎብኘታቸው ትክክለኛውን የቤተክር ስቲያኒቱን አስተምህሮ ሳያገኙ መቆየታቸውን የአካባቢው ምእመናን ለልኡካን ቡድኑ አባላት ሲገልጡ እንደነበር የተናገሩት ዲ/ን ምትኩ፤ መርሐ ግብሩ በተከታታይ ሊካሔድ እንደሚገባ መጠየቃቸውንም አስረድተዋል፡፡
ማኅበሩ በእነዚህ አካባቢዎች መዋቅሩን በማጠናከር የቅድስት ቤተክርስቲያንን ሥርዓትና መመሪያ አክብረው ከሚንቀሳቀሱ መምህራነ ወንጌል እና ዘማሪያን ጋር በመተባበር ደጋግሞ ወደ ስፍራው ሐዋርያዊ ጉዞ ማድረግ ይገባል፡፡ በዚህ አካባቢ ትኩረት ሰጥቶ በተከታታይ የተጠናከረ አገልግሎት መስጠትና ትምህርተ ወንጌል የተጠማውን ሕዝብ በማስተማር የቅድስት ቤተክርስቲያንን ተልዕኮዋን ይበልጥ ውጤታማ ለማደረግ መነሣሣት እንደሚያስፈልግ ዲ/ን ምትኩ ተናግረዋል፡፡

 
 /ምንጭ፦ ስምዐ ጽድቅ ከመጋቢት 1-15 ቀን 2003 ዓ.ም/

የደብረ ጽጌ ቅዱስ ዑራኤል ቤተ ክርስቲያን አካባቢ ወጣቶች መንፈሳዊ የአገልግሎት ማኅበር ዓመታዊ በዓሉን አከበረ፡፡

በኅሩይ ባየ
በአዲስ አበባ ሃገረ ሰkidusuraeal.jpgብከት በደብረ ጽጌ ቅዱስ ዑራኤል አጥቢያ ዐሥራኹለት ቀበሌዎች የሚኖሩ ወጣት የቤተ ክርስቲያን ልጆች የካቲት 20 ቀን 2003 ዓ. ም በደብረ ፅጌ ቅዱስ ዑራኤል ቤተ ክርስቲያን የሰንበቴ አዳራሽ መንፈሳዊ የአገልግሎት ማኅበራቸው የተመሠረተበትን አንደኛ ዓመት አከበሩ፡፡ 
ቁጥራቸው ከአንድ ሺሕ በላይ የሆኑት እነዚህ ወጣቶች በአንድ ዓመት ቆይታቸው በየወሩ በተለያዩ አዳራሾች እየተሰበሰቡ ኦርቶዶክሳዊ የሃይ ማኖት ትምህርት ሲማሩ መቆየታቸውን የማኅበሩ ሰብሳቢ ወጣት ተስፋዬ አዳነ ገልጧል፡፡
 
«የቤተ ክርስቲያንን ሥርዓት በጠበቀና በተደራጀ መልኩ፤ ትምህርተ ሃይማኖትን ለመማርና በመልካም ሥነ ምግባር ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል መዋቅርና አሠራሯን ጠብቆ በቤተ ክርስቲያን ቅጽር ግቢ መሰባሰብ የበለጠ ጠቀሜታ እንዳለው ይታመ ንበታል፡፡ ስለዚሀ በአጥቢያችን በደብረ ጽጌ ቅዱስ ዑራኤል ቤተ ክርስ ቲያን እየተገኘን መሰብሰብ ጀምረናል፡፡» ሲል የገለጠው ወጣት ተስፋዬ አዳነ፤ ወጣቶቹ በየሳምንቱ በአቅራቢያቸው ቤተ ክርስቲያን እየተገኙ ስብከተ ወንጌል መርሐ ግብሮችን እንደሚከታተሉና በወር አንድ ጊዜ ደግሞ በደብረ ጽጌ ቅዱስ ዑራኤል ቤተ ክርስቲያን አጠቃላይ ጉባኤያቸውን በማካሔድ የመዝሙር ጥናት እንዲሁም የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት እንደሚማሩ ተናግሯል፡፡

ማኅበሩ በ2002 ዓ. ም ተመሥርቶ አገልግሎቱን መስጠት ከጀመረበት ጊዜ አንሥቶ በርካታ መንፈሳዊ ተግባ ራትን እያከናወነ ይገኛል፡፡ ከተከናወኑት ተግባራት መካከል ጥቂቶቹ በእስር ቤት ያሉ ወገኖቻችን በዓል ጥምቀትን አስበው እንዲውሉ የምሣ ግብዣ ማዘጋጀት፤ የቤተ ክርስቲያን ዓመታዊ በዓላት ኦርቶዶክሳዊ ትውፊቶችን ሳይለቁ እንዲከበሩ የግንዛቤ ማስጨ በጪያ ትምህርት ማካሔድ፤ ወጣቶች በቤተ ክርስቲያን ሥርዐት መሠረት ታቦተ ሕጉን አጅበው የንግሥ በዓላትን እንዲያከብሩና የሚጠበቅባቸውን አገል ግሎት እንዲያበረክቱ በማድረግ ካከናወኗቸው ተግባራት ጥቂቶች እንደሆኑ በዕለቱ የቀረበው ሪፖርት ያስረዳል፡፡

ማኅበሩ በቀጣዩ የሥራ ጊዜ ካቀዳቸው ተግባራት ዋናዋናዎቹ፤ በቤተ ክርስቲያናችን የተቀጣጠለውን ውጫ ዊና ውስጣዊ ፈተና ለመቋቋም ዋናው መሣሪያ ጸሎት ስለሆነ በሳምንት አንድ ቀን የማኅበር ጸሎት ማድረስ፤ በተጀመረው የዐቢይ ጾም ወራት እያንዳንዱ የማኅበሩ አባል ቁርሱን ለነዳያን እንዲሰጥ ማድረግ፤ በምግብና በልብስ እጦት ምክንያት ከእናት ቤተ ክርስቲያናቸው ወደ ሌላ የእምነት ተቋም እንዳይፈልሱ አሳዳጊ አልባ የሆኑ ሕፃናትን እና ጧሪ ያጡ አረጋውያንን በግልና በቡድን መርዳት፤ በትምህርተ ሃይማኖት እውቀት ማነስ ምክንያት ወጣቶች በነጣቂ ተኩላ እንዳይወሰዱ ከአጥቢያቸው የሰበካ ጉባኤ እና ከሰንበት ትምህርት ቤት ጋር በመተባበር የቤተ ክርስቲያንን ትምህርተ ሃይማኖት ሥርዐት፣ ታሪክና ትውፊት ትምህርቶች እንዲከታተሉ ሁኔታዎችን ማመቻቸት እና በቤተ ክርስቲያን ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያበረከቱ ደጋግ አባቶችን በዓለ ልደታቸውን እና ዕረፍታቸውን ማክበር በሁለት ወር አንድ ጊዜ የሚታተም መንፈሳዊ መጽሔት ማዘጋጀት ዋና ዕቅዳቸው መሆኑን ወጣት ተስፋየ አዳነ ገልጧል፡፡

 
/ምንጭ፦ ስምዐ ጽድቅ ከመጋቢት 1-15 ቀን 2003 ዓ.ም/

ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን ያልጠበቀ ጉባኤ በወሊሶ ተካሄደ።

በተ/ሥላሴ ጸጋ ኪሮስ

መጋቢት 1፣ 2003 ዓ.ም

በምዕራብ ሸዋ ሃገረ ስብከት በወሊሶ ከተማ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን  ሥርዓትና ቀኖና ውጪ የሆነ ጉባኤ ተካሄደ።

ከየካቲት 25 እስከ 27፣ 2003 ዓ.ም ባሉት ቀናት የተካሄደው ጉባኤ ምእመናንን ለመጠበቅና ለማጽናት በ ሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ጥሪ የተዘጋጀ ቢሆንም በጉባኤው ማለቂያ ቀን ከቀኖና ቤተ ክርስቲያን ውጭ በዐቢይ ፆም መዝሙር በከበሮና በጭብጨባ ሊቀ ጳጳሱ በተገኙበት ሲዘመር እንደነበር ታውቋል።
ከማኅበረ ቅዱሳን መካነ ድር ጋር አጭር ቆይታ ያደረጉት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን የሊቃውንት ጉባኤ አባል የሆኑት ሊቀ ካህናት ክንፈ ገብርኤል አልታየ “በቀኖና ቤተ ክርስቲያን መሠረት በዐቢይ ፆም ማኅሌት አይቆምም፣ ከበሮ አይመታም፣ ጸናጽል አይንሿሿም፣ እልልታም የለም። ስብሐተ እግዚአብሔር የሚደርሰውም በዘንግ /በመቋሚያ/ ብቻ ነው፤ በዝማሜ። የሚቆመውም ፆመ ድጓና የፆም ምዕራፍ ነው።” በማለት ሥርዓቱን ያብራራሉ።
እሑድም ቢሆን የመወድስ አደራረስ እንዳለና ቅኔም በየምዕራፉ እንደሚደረግ፥ ማኅሌት ግን እንደማይቆም፣ ከበሮም እንደማይመታ ጨምረው ያስረዳሉ።
በቅዱስ ሲኖዶስ በተወሰነው መሠረት በዐቢይ ፆም መሐል ከሚውሉ ክብረ በዓላት ውጭ ማኅሌት መቆም፣ ከበሮ መምታትና ማጨብጨብ እና ሌሎች ደስታን የሚፈጥሩ ነገሮችን ማድረግ ክልክል ነው።
ይህንንም ብያኔ ለማሻሻል የሚችለው ቅዱስ ሲኖዶስ ብቻ መሆኑን የሚገልጹት ሊቀ ካህናት ክንፈ ገብርኤል አንድ ሀገረ ስብከት በተናጠል ሥርዓት መለወጥ እንደማይችልም አስረግጠው ይናገራሉ።
በጉባኤው የነበሩ በርካታ ምእመናን በነበረው የሥርዓት መፋለስ ማዘናቸውንና በጉባኤው ላይ የተሰጡ ትምህርቶችም ብቁ ያልነበሩና የታለመውን ግብ ይመታሉ ብለው እንደማያምኑ ገልጸዋል።

የዓለም ከተማ ወረዳ ማዕከል ያሠራውን ጽሕፈት ቤት አስመረቀ።

በተስፋዬ አእምሮ
 የካቲት 29፣2003 ዓ.ም

በሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት የዓለም ከተማ ወረዳ ማዕከል ያስገነባውን ጽሕፈት ቤት የካቲት 13 ቀን 2003 ዓ.ም  አስመረቀ፡፡ 

የወረዳ ማዕከሉ ሰብሳቢ ወ/ሪት ሰላማዊት ፍስሐ በምረቃ መርሃ ግብሩ ላይ እንደገለጹት ወረዳ ማእከሉ ከተቋቋመበት ከ1992 ዓ.ም ጀምሮ የራሱ የሆነ ጽሐፈት ቤት አልነበረውም። የተለያዩ መረጃዎችም በአባላት እጅ ይቀመጡና ለጥፋት ይጋለጡ እንደነበር አስታውሰው ይኸን ችግር ለመቅረፍ የማእከሉ ጽሕፈት ቤት የሚገነባበት ቦታ ለማግኘት ለቅዱስ አማኑኤል ቤተ ክርስቲያን ሰበካ ጉባኤ ጥያቄ ቀርቦ በሰበካ ጉባኤው መልካም ፈቃድ ከ2001 ዓ.ም ጀምሮ የገንዘብ ማሰባሰብና የግንባታ ሥራው ተጀምሮ አሁን ለምረቃ በቅቷል ብለዋል፡፡

የጽሕፈት ቤቱ መገንባት የማዕከሉን አገልግሎት ለማፋጠን ከፍተኛ ድርሻ የሚኖረው ሲሆን ለጽሕፈት ቤቱ ሥራ የወጣው ወጪ ፣ ዘጠኝ ሺ ስድስት መቶ አርባ ስምንት ብር ከበጎ አድራጊዎች፣ አርባ ሦስት ሺ ሰባት መቶ ሰላሳ ስድስት ብር ከአባላት እንዲሁም ሁለት ሺ ብር ከእድር የተገኘ ሲሆን በድምሩ 55,384.00 ብር /በሃምሳ አምስት ሺህ ሦስት መቶ ሰማንያ አራት ብር/ መሆኑንና በአጠቃላይ 95 ከመቶ ግንባታው በአባላት፣ በምዕመናንና በግቢ ጉባኤያት ተሳትፎ እንደተከናወነ የደብረ ብርሃን ወረዳ ማዕከል ያደረሰን መረጃ ይጠቁማል፡፡

በዕለቱ ጥሪ የተደረገላቸው የገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎች፣ የወረዳ ማዕከሉ አባላት፣ የደብረ ብርሃን ማዕከልና የዋና ማዕከል ተወካዮች ተገኝተዋል፡፡

የቅድስት አርሴማ ጽላት በቁፋሮ ተገኘ።

 በተስፋዬ አእምሮ
 የካቲት 29፣2003 ዓ.ም
የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት አንጎለላና ጠራ ወረዳ በቂጣልኝ ቀበሌ የቅድስት አርሴማ ጽላት በቁፋሮ ተገኘ፡፡
 
ጽላቱ አባ ኃይለ ሥላሴ ለማ በተባሉ አባት አስተባባሪነት ዋሻ ውስጥ የተገኘ ሲሆን፥ ዋሻው በግራኝ ወረራ ዘመን የተዘጋ እንደሆነ ይታመናል፡፡ 
 
ከዚህ በፊት በዋሻው ውስጥ የተለያዩ ቅርሶች የተገኙ ሲሆን ሌሎች ቅርሶችን ለመፈለግ ቁፋሮ ሲካሄድ ይህ ጽላት እንደተገኘ ለቅርሱ እውቅና የሰጡት የአካባቢው ባሕልና ቱሪዝም ቢሮ እና ማኅበራዊ ፍርድ ቤት አረጋግጠዋል፡፡

የወረዳው ቤተ ክህነትና የኩሉ ወይን ቅዱስ ጊዮርጊስ ሰበካ ጉባኤም ለሚመለከታቸው አካላት እንዳሳወቁና በአሁኑ ጊዜም ጽላቱ ወደ ሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ተወስዶ እንዲባረክና አገልግሎት መስጠት እንዲጀምር ለማድረግ ምእመናን በዝግጅት ላይ መሆናቸውን የደብረ ብርሃን ማዕከል ያደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡

ቅድስት(የዐቢይ ጾም ሁለተኛ ሳምንት)

የዕለተ ሰንበት መዝሙር (ከጾመ ድጓ)

ግነዩ ለእግዚአብሔር ወጸውዑ ስሞ ወንግርዎሙ ለአሕዛብ ምግባሮ ሀቡ ስብሐተ ለስሙ አክብሩ ሰንበተ ተገበሩ ጽድቀ ዝግቡ ለክሙ መዝገበ ዘበሰማያት ኅበ ፃፄ ኢያማስኖ ወኢይረክቦ ሰራቂ ድልዋኒክሙ ንበሩ ዘበላዕሉ ጸልዩ ኀበ ሀሎ ክርስቶስ
ትርጉም: ለእግዚአብሔር ተገዙ ስሙንም ጥሩ ሥራውንም ለአሕዛብ ንገሯቸው ለስሙም ምስጋናን ስጡ /አቅርቡ/ ሰንበትን አክብሩ እውነትንም አድርጉ ብል የማያበላሸው ሌባም የማያገኘው በሰማያት ያለ መዝገብን ለእናንተ ሰብስቡ፤ ተዘጋጅታችኹም ተቀመጡ ክርስቶስ ወዳለበት ወደላይ አስቡ፡፡

ምንባባት
መልዕክታት
1ኛ ተሰ.41-12 አሁንም ወንድሞቻችን ሆይ በእኛ ዘንድ እንደ ታዘዛችሁ በሚገባ ትሄዱ ዘንድ እግዚአብሔርንም ደስ ታሰኙ ዘንድ ደግሞ እንደ ሄዳችሁ ከፊት ይልቅ በዚሁ ታበዙና ትጨምሩ ዘንድ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ እንነግራችኋለን፤ እንማልዳችኋለንም፡፡ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስም ያዘዝናችሁን ትእዛዝ ታውቃላችሁ፡፡(ተጨማሪ ያንብቡ)
1ኛጴጥ.1·13-ፍጻ.ስለዚህ የልቡናችሁን ወገብ ታጥቃችሁና ነቅታችሁ ኑሩ፤ ኢየሱስ ክርስቶስም ሲገለጥ የምታገኙትን ጸጋ ፈጽማችሁ ተስፋ አድርጉ፡፡ (ተጨማሪ ያንብቡ)
ግብረ ሐዋርያት
የሐዋ.10·17-29. ጴጥሮስም ስለ አየው ራእይ ምን እንደሆነ ሲያወጣና ሲያወርድ ከቆርኔሌዎስ ተልከው የመጡ ሰዎች የስምዖንን ቤት እየጠየቁ በደጅ ቁመው ነበር፡፡ (ተጨማሪ ያንብቡ)
ምስባክ
መዝ.95·5 እግዚአብሔርሰ ሰማያተ ገብረ አሚን ወሠናይት ቅድሜሁ ቅድሳት ወዕበየ ስብሐት ውስተ መቅደሱ

ትርጉም፦እግዚአብሔር ግን ሰማያትን ሠራ ምስጋና ውበት በፊቱ ቅዱሰነትና ግርማ በመቅደሱ ውስጥ ናቸው፡፡

ወንጌል
ማቴ.6·16-24 €œበምትጾሙበት ጊዜ እንደ ግብዞች አትጠውልጉ፤ እነርሱ እንደ ጾሙ ለሰው ይታዩ ዘንድ መልካቸውን ይለውጣሉና እውነት እላችኋለሁ ዋጋቸውን ተቀብለዋል፡፡ (ተጨማሪ ያንብቡ)
ቅዳሴ
ዘኤጲፋንዮስ

 

ሰበር ዜና

(ሐሙስ የካቲት 24  2003 ዓ.ም. )
ብፁዕ አቡነ ይስሐቅ አረፉ።
የቀድሞው የጠቅላይ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅና የባሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የነበሩት ብፁዕ አቡነ ይስሐቅ አረፉ። abune yishaqe.jpg
 
በድንገተኛ ህመም ሳቢያ ወደ ባልቻ ሆስፒታል ለሕክምና በመሄድ ላይ ሳሉ እንዳረፉ ለማወቅ ተችሏል።
 
አስከሬናቸው ከሚገኝበት ከባልቻ ሆስፒታል ነገ የሚወጣ ሲሆን ቀብራቸውም የፊታችን ቅዳሜ  ይፈጸማል ተብሎ ይጠበቃል።

7ኛው ሀገር አቀፍ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት /ግቢ ጉባኤያት/ ሴሚናር ነገ ይጀመራል፡፡

(ሐሙስ የካቲት 24  2003 ዓ.ም. ) 
በእንዳለ ደጀኔ
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰ/ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን 7ኛውን የግቢ ጉባኤያት ተወካዮች ሴሚናር ከየካቲት 25-27 ቀን 2003 ዓ.ም አዲስ አበባ ላይ እንደሚያካሄድ አስታወቀ፡፡

የግቢ ጉባኤያት ማደራጃና ማስተባበሪያ ክፍል ሓላፊ ዲ/ን ተ/ብርሃን ገ/ሚካኤል እንደገለጹት በሴሚናሩ 310 የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት /የግቢ ጉባኤያት/  ተወካዮች የ41 ማእከላትና ወረዳ ማእከላት የግቢ ጉባኤያት ማደራጃና ማስተባበሪያ ክፍል ሓላፊዎች ይገኛሉ፡፡

ሴሚናሩም ማኅበሩ በ1984 ዓ.ም በቅዱስ ሲኖዶስ ጸድቆ በተሰጠው መተዳደሪያ ደንብ መሠረት በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት /ግቢ ጉባኤያት/ የሚገኙ የቤተ ክርስቲያን ልጆች በማስተማርና ለቤተ ክርስቲያን ተተኪ ትውልድ እንዲሆኑ ለማብቃት እየሠራ መሆኑን የሚያሳይ ነው፡፡

ሴሚናሩ በሚካሄድባቸው 3 ቀናት በሀገሪቱ ካሉ የከፍተኛ ተቋማት የግቢ ጉባኤያት ተወካዮች ሴሚናር ላይ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የልምድ ተሞክሮ፣ የአገልግሎት ስልትና መንፈሳዊ ሕይወት እንዲሁም በምግባረ ሰናይ ያላቸውን ተሳትፎ አጠናክረው የሚሔዱበትን አቅጣጫ መንደፍ የሚያስችል ውይይት እንዲደረግ ይጠበቃል፡፡

የግቢ ጉባኤያት ሴሚናር፣ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተመርቀው የሚወጡ ተማሪዎች ቤተ ክርስቲያናቸውንና ሀገራቸውን በጥሩ ሥነ-ምግባርና በታማኝነት በተማሩበት ሙያ ለማገልገል የሚያስችል የተለያዩ የአገልግሎት ስልቶችን የሚረዱበት፣ ራዕይ ያላቸው፤ በገንዘባቸው፣ በዕውቀታቸውና በጉልበታቸው አስተዋጽኦ ሊያበረክቱ የሚችሉበትን አቅጣጫ የሚያውቁበት ሲሆን፣ ከተቋማቸው ማኅበረሰብ፣ ከአጥቢያ ሰ/ት/ቤቶችና ሰ/ጉባኤያት ጋር በመሆን የቤተ ክርስቲያንን ሁለንተናዊ አገልግሎት ለመፈፀም የሚዘጋጁበት እንደሚሆን ሓላፊው ገልፀዋል፡፡

ማኅበሩ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሥር ከተቋቋመበት ከ1984 ዓ.ም ጀምሮ፣ ዓለም አቀፍ መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት በመስጠት ላይ የሚገኝ ሲሆን በአሁኑ ወቅት በሥሩ የሚገኙ ከ120.000 በላይ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎችን የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት እያስተማረ ይገኛል፡፡

ለ7ኛ ጊዜ በተዘጋጀው በዚሁ የግቢ ጉባኤ ተወካዮች ሴሚናር ቅዱስ ፓትሪያሪኩን ጨምሮ ሊቃነ ጳጳሳት፣ የጠቅላይ ቤተክህነት የመምሪያ ሓላፊዎች፣ የአዲስ አበባ ሃ/ስብከት የመምሪያ ሓላፊዎችና ጥሪ የተደረገላቸው የክብር እንግዶች ይገኛሉ፡፡

መጋቢት 11 ሲምፖዚየም

2011-1.jpg

ከ400 በላይ የጉምዝ ብሔረሰብ አባላት ተጠመቁ።

በሪሁን ተፈራ ከባህር ዳር ማዕከል
በምዕራብ ጎጃም ሀገረ ስብከት ወንበርማ ወረዳ የሚገኙ ከ400 በላይ የሚሆኑ የጉምዝ ብሔረሰብ አባላት በጎመር ቅድስት ክርስቶስ ሰምራ ቤተክርስቲያን እሑድ  የካቲት 13 ቀን 2003 ዓ.ም በብፁዕ አቡነ በርናባስ የምዕራብ ጎጃም ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ በሀገረ ስብከቱ ቆሞሳትና ካህናት መጠመቃቸውን የማኅበረ ቅዱሳን ባህር ዳር ማዕከል ገለጸ፡፡

 
ብፁዕ አቡነ በርናባስ የካቲት 12ቀን 2003 ዓ.ም ከቀኑ በ10፡40 ሰዓት ጎመር ሲደርሱ  የወረዳው ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅና ሌሎች ሠራተኞች፣ የማኅበረ ቅዱሳን ባሕር ዳር ማዕከል፣ የሽንዲ ወረዳ ማዕከል አባላት፣ የአካባቢው ሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች፣ ምእመናን እና የጉምዝ ብሔረሰብ አባላት፣ በመዝሙርና በእልልታ የታጀበ ደማቅ አቀባበል አድርገውላቸዋል፡፡
akebabele.jpg

ከዚህ በተጨማሪም በዕለቱ የማኅበረ ቅዱሳን ሽንዲ ወረዳ ማዕከል አባላት፣ የኮሊ ኢየሱስ ቤተክርስቲያን መዘምራን፣ የሸንዲ ደብረ ብሥራት ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስቲያን መዘምራን፣ ጎመር ቅድስት ክርስቶስ ሰምራ ቤተክርስትያን ሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎች መዝሙርና ሥነ ጽሑፍ በኦሮምኛ በአማርኛ ቋንቋ ለምእመናን አቅርበዋል፡፡

Abune Bernabas Siatemku.jpgሥርዓተ ጥምቀቱ ከሌሊቱ 10፡00 ሰዓት የተጀመረ ሲሆን የተጠመቁት ምእመናን በሥርዓተ ቅዳሴው ተሳትፈው ሥጋ ወደሙ ከተቀበሉ በኋላ በሊቀ ማዕምራን ሀዲስ ጤናው የሀገረ ስብከቱ ስብከተ ወንጌል ክፍል ኃላፊ እና በመጋቤ ምሥጢር ኃይለማርያም ታዬ ትምህርት ተሰጥቶ ሀገረ ስብከቱ ለተጠማቂያን የብሔረሰቡ አባላት 600 የአንገት መስቀል አበርክቷል፡፡

ተጠማቂ  ምእመናኑ አባይ በረሃን ከሚያዋስኑ ከወንበርማ ወረዳ ሦስት ቀበሌዎች የመጡ ሲሆኑ በአካባቢው ከአፄ ኃ/ሥላሴ ዘመነ መንግሥት በፊት ጀምሮ የተሠሩ አብያተ ክርስቲያናት አልፎ አልፎ ያሉና የተጠመቁ የብሔረሰቡ ምእመናን ቢኖሩም ለዚህ በርካታ  የብሔረሰቡ አባላት መጠመቅ ምክንያት የሆኑት አቶ አያና የተባሉ የቻግኒ ወረዳ ማዕከል አባል ወደ ቦታው ለሥራ በመጡና አሁን የተዛወሩት ግለሰብ እና መምህርት መድኃኒት ሞላ የሽንዴ ወረዳ ማዕከል አባል አማካኝነት እንደሆነ ተገልጿል፡፡

የሽንዲ ወረዳ ማዕከል በ1994 ዓ.ም ሁለት ህፃናትን ከአካባቢው በመውሰድና የአብነት ትምህርት ቤትYewerwda Maekelu Meketel sebsabi Betemeherte laye.jpg ለማስገባት የጀመረው ሙከራ ልጆቹ ሊለምዱ ስላልቻሉ ቢቋረጥም ለዚህ እንቅስቃሴ መጠናከር በምዕራብ ጎጃም ሀገረ ስብከት ወንበርማ ወረዳ ቤተክህነት እና ከአካባቢው ሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች ጋር በመሆን 2000 ዓ.ም ግንቦት 16 ቀን ወደ የማቤል ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ቤተክርስቲያን በወረዳ ማዕከሉ አስተባባሪነት የተደረገ የእግር ጉዞና ከአካባቢው የጎሳ አካላት ጋር የተደረገው ትምህርትና ውይይት ትልቅ በር እንደከፈተና ከዚያም በኋላ በወረዳ ቤተክህነቱ እና ወረዳ ማዕከሉ የሚደረጉ ትምህርተ ወንጌል ይበልጥ ግንኙነታቸውን እንዳጠናከረው ለማወቅ ተችሏል፡፡

የባህርዳር ማዕከል እና ሽንዲ ወረዳ ማዕከል በሽንዲ ከተማ የእራት ግብዣ በማዘጋጀትና ከበጎ አድራጊዎች 4000 ብር አስባስቦ ቆርቆሮ እና እንጨት ገዝቶ በማጓጓዣ፤ ግንቦት 2002 ዓ.ም ጉባኤ በማካሄድና ከ460 በላይ የብሔረሰቡ አባላት ጋር ውይይት አድርጎ በቀበሌው ባሉት በመምህርት መድኃኒት ሞላና አንድ ሌላ መምህር አስተባባሪነት ተጨማሪ እንጨት እንዲያዋጡ በማድረግ ቤተክርስቲያን በጎመር ቀበሌ ሊሠራ ችሏል፡፡

ብፁዕ አቡነ በርናባስ ከአሁን በፊት የተጠመቁትንና አዲስ ተጠማቂያንን እንዲበረቱ መክረው በበዓሉ ለተገኙ ምዕመናን እንዳሉት “የእግዚአብሔር ፈቃድ ስለሆነ ወገኖቻችን ወደዚህች ሃይማኖት ሊመጡ ችለዋል፡፡ ስለዚህ ሁላችንም በደስታ ልንቀበላቸው፣ ልንከባከባቸውና ልንደግፋቸው ይገባል”፡፡ ሲሉ አሳስበዋል፡፡

የብሔረሰቡ አባላት በበኩላቸው ከ 2፡00-4፡00 ሰዓት የሚፈጅ የእግር ጉዞ ተጉዘው  እንደተጠመቁ በመግለጽ ለሰሩት ቤተክርስቲያን ጽላት እንዲገባላቸው፣ በቅርብ ቦታ ተጨማሪ አብያተ ክርስቲያናት እንደሰሩላቸውና ካህናት እንዲመደቡላቸው ጠይቀዋል፡፡ ብፁዕ አቡነ በርናባስም ከወረዳ ቤተክህነት ጋር በመሆን የተቻላቸውን እንደሚፈጽሙና ምዕመናን ከጎናቸው በመሆን ለቤተክርስቲያን ሥራ እንዲተጉ ጠይቀዋል፡፡ በመጨረሻም በብፁዕነታቸው ጸሎትና ቡራኬ ጉባኤው ተጠናቋል፡፡

 ረድኤተ እግዚአብሔር አይለየን።