ጉባኤው ባለ 26 ነጥብ የአቋም መግለጫና የውሳኔ ሐሳብ አሳለፈ

ለቤተክርስቲያን ልማት የላቀ አስተዋጽኦ ያበረከቱ ተሸለሙ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ 28ኛው አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ባለ 26 ነጥብ የጋራ የአቋም መግለጫና የውሳኔ ሐሳብ በማቅረብ ተጠናቀቀ፡፡

ከጥቅምት 6-11 ቀን 2002 ዓ.ም ሲካሔድ የሰነበተው ይህ ስብሰባ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳዉሎስ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ፕሬዚዳንት የዓለም ሃይማኖቶች የክብር ፕሬዚዳንት በሀገር ውስጥና በወጪ ሀገር የሚገኙ ሊቃነ ጳጳሳት፣ የየአህጉረ ስብከቱ የሥራ ሓላፊዎች፣ የምእመናንና የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች በተገኙበት ነው፡፡

ጉባኤውን በጸሎት የከፈቱት ቅዱስነታቸው፤ የቤተክርስቲያን ዓላማ ሰላም በመሆኑ በሥልጡንና ሰላማዊ በሆነ መንገድ ጉባኤውን ማካሔድ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡ «ሰላማዊ በሆነ መንገድ የሚካሔድ ውይይት የጎደለን ይሞላል የተጣመመን ያቃናል» ያሉት ቅዱስነታቸው «ቤተክርስቲያናችንን በልማቱ ለማሳደግ ጠንክሮ መሥራት ያስፈልጋል» በማለት ጉባኤውን አስጀምረዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ይስሐቅ የጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅና የባሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በ2001 ዓ.ም በጠቅላይ ቤተክህነቱና በየአህጉረ ስብከቶች የተከናወኑትን ዐበይት ጉዳዮች የተመለከተውን ዘገባ በንባብ አሰምተዋል፡፡

ዘገባውን ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ በሐዋርያት ሥራ በጻፈው መልእክት /ም.5-42/ የጀመሩት ሥራ አስኪያጁ፤ ለቤተክርስቲያን የደም ሥር፣ ለምእመናን የጀርባ አጥንት የሆነው ስብከተ ወንጌልን በስፋትና በአግባቡ እንዲሰበክ፤ ምእመናን በእምነታቸው እንዲጸኑ፣ በሥነ ምግባር እንዲጎለብቱ፣ ከባዕድ ሃይማኖት ራሳቸውንና ቤተሰቦቻቸውን እንዲጠብቁ፣ ሰበካ ጉባኤያት እንዲስፋፉና እንዲጠናከሩ፣ የልማትና የምግባረ ሠናይ ሥራዎች እንዲሠሩ፣ ድህነትና ድንቁርና ከሕዝባችን ጫንቃ እንዲወርዱ ለማድረግ ሁሉም ጥረት ማድረግ ወቅቱ የሚጠይቀው ዐቢይ ተግባር መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ዓመታዊ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ በዚህ ሁኔታ ሲካሔድ ሃያ ስምንተኛ ዓመቱን መያዙን የተናገሩት ብፁዕ አቡነ ይስሐቅ «ጉባኤው ከወጣኒነት ወደ ፍጹምነት መሸጋገር እንደሚኖርበት የሁላችንም እምነት ነው፡፡» ብለዋል፡፡ ስለሆነም መለኪያው ከማእከል እስከ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት የሚቀርበው ዘገባና ውጤት ተኮር ሥራ ተሠርቶ ሲገኝ ብቻ መሆኑን አመልክተው፤ ይህ ካልሆነ ግን በየዓመቱ የሚደረገው ስብሰባ ልማዳዊ እንዳይሆን በብርቱ ማጤን እንደሚገባ አስገንዝበዋል፡፡

በመቀጠልም ሥራ አስኪያጁ ለግምገማና ለውይይት እንዲያመች ከብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽ/ቤት፣ ከመንበረ ፓትርያርከ ጠቅላይ ጽ/ቤት፣ ከየአህጉረ ስብከቱ ጽ/ቤቶች በ2001 ዓ.ም የተከናወነውን የሥራ ክንውን ዘገባ አቅርበዋል፡፡

የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽ/ቤትን በተመለከተው ዘገባ ቅዱስ ፓትርያርኩ በሀገር ውስጥና በውጪ ሐዋርያዊ አገልግሎትና ልዩ ልዩ የሥራ ክንውኖችን ማድርጋቸውን አመልክቷል፡፡ ከነዚህ  ውስጥ ሐምሌ 22 ቀን 2000 ዓ.ም የቀድሞ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ቢል ክሊንተን የቅዱስ ላሊበላን ታሪካዊ መካናት እንዲጎበኙ መደረጉና በኋላም ከቅዱስ አባታችን ጋር ተወያይተው ለቤተክርስቲያናችን አድናቆት መቸራቸው ገልጸዋል፡፡ ነሔሴ 29 ቀን 2000 ዓ.ም ቅዱስ አባታችን የሀገሪቱ ፕሬዚዳንትና ልዩ ልዩ የሀገር ውስጥና የውጪ ሀገር እንግዶች በተገኙበት ከጣሊያን መጥቶ አክሱም በቀድሞ ቦታው በተተከለው የአክሱም ሐውልት ሥነ ሥርዓት ላይ በክብር መገኘታቸው ተጠቅሷል፡፡

በመስከረም 13 ቀን 2001 ዓ.ም በኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት በናዝሬት ቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን የተሠራውን ሕንፃ መመረቃቸው፣ መስከረም 24 ቀን 2001 ዓ.ም በምዕራብ ሸዋ አምቦ በጃን መንግሥት የተሠራውን ትምህርት ቤት ምረቃ ወቅት መገኘታቸውና መስከረም 16 ቀን 2001 ዓ.ም የሚከበረውን የመስቀል ደመራ በዓል በበለጠ ተጠናክሮ እንዲውል ጉዳዩ ለሚመለከተው አመራር መስጠታቸው በዘገባው ተመልክቷል፡፡

በቅዱስነታቸው ሰብሳቢነት የተመራው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ስብሰባ የተለያዩ አጀንዳዎች ላይ ተወያይቶ ውሳኔ እንዲያስተላልፍ ሁኔታዎች መመቻቸታቸው፣ በቅዱስነታቸው መመሪያ ሰጪነት ሸንኮራ ዮሐንስን ጨምሮ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የሚገኙና አዳዲስ አብያተ ክርስቲያናትና ቅዳሴ ቤት ተገኝተው እንዲከበር መደረጉ ተጠቅሷል፡፡

ልዑል አክሊለ ብርሃን መኮንን ኃይለ ሥላሴ የተባሉ በጎ አድራጊ ለቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ግንባታ የሚውል አንድ ሚሊዮን፣ ለአክሱም ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተመጻሕፍት ወቤተመዘክር የሚውል አምስት መቶ ሺሕ ብር እርዳታ ሲለግሱ ቅዱስነታቸው በመገኘት ርዳታው ለተሰጣቸው ማስረከባቸው በልዩ ጽ/ቤቱ የተሠሩ ዐበይት ጉዳዮች መሆናቸው በሪፖርቱ ተመልክቷል፡፡

በውጪ ሀገርም በቅዱስነታቸው የተመረጡ ልዑካን ከኅዳር 5-16 ቀን 2001 ዓ.ም ድረስ ቦነስአይረስ በተካሔደው ዓለም አቀፍ ጉባኤ ላይ መሳተፍ፣ ከስብሰባው መልስም በሶርያ በመገኘት ከፕሬዝዳንቱ ዶ/ር በሽር አል አሳድ ጋር ስለ ዓለም ሰላም ጉዳይ መወያየታቸው፣ ከሶርያም ወደ ሊባኖስ በመጓዝ በቤሩት በሚገኙ ምእመናን የተገነባውን ቤተ ሳይዳ ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስቲያን በመገኘት ሕንፃውን ባርከው ቅዳሴ ቤት መክበሩ፤ እንዲሁም ወደ ግብጽ በማምራት ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሺኖዳ ሳልሳዊ እስክንድርያ ሊቀ ጳጳስ ጋር በሁለቱ አኃት አብያተ ክርስቲያናት ግንኙነት መወያየታቸው በውጪው ዓለም ካከናወኑት ዐበይት ጉዳዮች መካከል ይጠቀሳሉ፡፡

ስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልዕኮ በተመለከተ ዋና ሥራ አስኪያጁ ባቀረቡት ዘገባ፤ በዋናው መሥሪያ ቤት ያሉትን ሰባክያነ ወንጌልንና በሰዋሰው ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ፣ በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ በአዲስ አበባ የሚገኙትን ጨምሮ በማስተባበር በ26 አህጉረ ስብከት የስብከተ ወንጌል ሥምሪት መደረጉን አስታውቀዋል፡፡

ስበከተ ወንጌልን ይበልጥ ለማስፋፋት እንዲረዳ በደቡብ ኦሞ፣ በሽሬ፣ በደቡብ፣ በሰሜንና በምዕራብ ወሎ፣ በሶማሌ፣ በወላይታና በዳውሮ፣ በጉራጌ፣ በምሥራቅ ሐረርጌ፣ በአዲግራት፣ አክሱም፣ በአፋርና በምሥራቅ ጎጃም አህጉረ ስብከት 1ሺሕ228 ያህል ሰባክያነ ወንጌል መመደባቸውንም ሥራ አስኪያጁ አብራርተዋል፡፡

ገቢና ወጪን አስመልክቶ ከቁልቢ ንዋየ ቅድሳት ማደራጃ ከስብከተ ወንጌል ጉባኤ አንድ በመቶ አስተዋጽኦና ከመጽሔት ሽያጭ 238¸616.77 ገቢ ሲሆን ጠቅላላ ወጪው ደግሞ 238¸325.52 መሆኑን ብፁዕ አቡነ ይስሐቅ አመልክተዋል፡፡

በሊቃውንት ጉባኤ በኩል በ2001 ዓ.ም ከቅዱስ ሲኖዶስ ጀምሮ ከአምስት የቤተክርስቲያናችን ክፍሎች፣ ከተወካዮች ምክር ቤት እና ከልዩ ልዩ ድርጅቶች፣ ከአራት የአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናትና አምስት ግለሰቦች የተዘጋጁ በድምሩ 192 የሆኑ በጥልቅ ታይተው እንዲታረሙ የተላኩትን ታላላቅ መጻሕፍት፣ መለስተኛ ጽሑፎችንና ጥያቄዎች ተመ ልክቶ ከአስተያየት ጋር ወደ በላይ አካል መመለሱን እንዲሁም ተጠቃሎ እንዲታተም የተጀመረውን የግእዝ መጽሐፍ ቅዱስ እያመሳከረ በመጀመሪያ የማጣራት ሥራ ላይ እንደ ሚገኝም ሥራ አስኪያጁ አስረድተዋል፡፡

ትምህርትና ማሠልጠኛን በተመለከተ ለ22 አህጉረ ስብከት አብነት ትምህርት ቤቶች አንድ ሚሊዮን 69 ሺሕ ብር፣ ለ14 አህጉረ ስብከት ንባብና ቅዳሴ ቤት 260 ሺሕ ብር፣ ለ21 አህጉረ ስብከት ካህናት ማሰልጠኛ 750 ሺሕ ብር በድምሩ 2 ሚሊዮን 79 ሺሕ ብር መላኩን ገልጸዋል፡፡

በጀትና ሒሳብን አስመልክተው ባቀረቡት ዘገባ ከቤተክርስቲያኒቱ የገቢ ርዕሶች 48 ሚሊዮን 631 ሺሕ 40 ብር ለማስገባት ታቅዶ 45 ሚሊዮን 711 ሺሕ 685 ብር ብቻ እንደተገኘና ከዚህም ውስጥ 39 ሚሊዮን 566 ሺሕ 487 ብር ወጪ ሆኖ በሥራ ላይ እንደዋለ አስረድ ተዋል፡፡

ጠቅላይ ቤተክህነቱ በስድስት መምሪያዎች እና በ10 የጠቅላይ ቤተክህነቱ ድርጅቶች፣ አራት አህጉረ ስብከቶችና የቁልቢ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ሒሳብ ተመርምሮ 387 ሚሊዮን 431 ሺሕ 782 ብር ገቢ፣ 344 ሚሊዮን 674 ሺሕ 313 ወጪ ሲሆን አራት ሺሕ 496 ብር ጉድለት መገኘቱን ብፁዕ አቡነ ይስሐቅ በዘገባቸው አመልክተዋል፡፡

በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ በኩል በ 2001 ዓ.ም ያሬዳዊ ዜማ የካሴትና የመጽሔት ሥርጭትን በተመለከተ ወጥ የሆነ ያሬዳዊ መዝሙር እንዲዘመር ጥረትና እንቅስቃሴ መደረጉን፣ ሐምሌ 5 ቀን 2000 ዓ.ም የተከበረውን የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ 16ኛ ዓመት በዓለ ሲመት ወጣቶችን የማስተባበር ሥራ መሠራቱን፣ ከነሐሴ 1-16 ቀን 2000 ዓ.ም ድረስ በጾመ ፍልሰታ ለማርያም ሱባኤ የሰንበት ትምህርት ቤት አባላት በየአብያተ ክርስቲያናቱ በመገኘት ተገቢውን መንፈሳዊ አገልግሎት እንዲሰጡ በመምሪያው በኩል ትእዛዝ መተላለፉን ዘገባው አመልክቷል፡፡

በተጨማሪም ማደራጃ መምሪያው መስከረም 1 ቀን 2001 ዓ.ም የዘመን መለወጫ በዓልን አስመልክቶ የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ የእንኳን አደረሰዎ በዓል ላይ የሰንበት ትምህርት ቤት አባላት አገልግሎት እንዲሰጡ መመሪያ ማስተላለፉንና፣ የመስቀል ደመራ በዓል በደማቅ መንፈሳዊ ሥነ ሥርዐት እንዲከበር የሰንበት ትምህርት ቤት አባላትን በማሠልጠን የሚጠበቀውን መንፈሳዊ አገልግሎት እንዲያበረክቱ ማድረጉን ሥራ አስኪያጁ ጠቁመዋል፡፡

በማኅበረ ቅዱሳን በኩል ደግሞ በዋናው ማዕከል አማካኝነት ብቻ ለ22 ሕዝባዊ ጉባኤያት፣ በዐሥር የተለያዩ የወረዳ ከተሞች ሐዋርያዊ ጉዞ መደረጉን፣ ስብከተ ወንጌል ካልደረሰባቸው ጠረፋማ አህጉረ ስብከት ለተውጣጡ 40 ወጣቶችና በዝዋይና በጅማ ካህናት ማሠልጠኛ 135 ልዑካን ሥልጠና መስጠቱን፣ ትምህርተ ሃይማኖት እና መንፈሳዊ መልእክት የያዙ 325 ሺሕ የስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 225 ሺሕ ሐመር መጽሔትና ሰባት ሺሕ ልዩ እትም ሐመረ ተዋሕዶ በ2001 ዓ.ም ማኅበሩ ማሰራጨቱን ሥራ አስኪያጁ በዘገባቸው ገልጸዋል፡፡

በተጨማሪም ማኅበሩ ልዩ ልዩ የቤተክርስቲያን ትምህርት የያዙ ዘጠኝ መጻሕፍትን በአማርኛና ኦሮምኛ ቋንቋዎች አሳትሞ ከ 57 ሺሕ ቅጂዎች በላይ ማሠራጨቱን፣ በድምፅና በምስል ልዩ ልዩ ወቅታዊነት ያላቸውን ጽሑፎች በአማርኛና በእንግሊዚኛ ቋንቋዎች በዌብሳይቱ /መካነ ድሩ/ ማስተላለፉን፣ በሀገር ውስጥ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተከታታይ ትምህርትና ሥልጠና መስጠቱ፣ ለአብነት ትምህርት ቤቶች 300 ደቀመዛሙርት የመሠረታዊ ትምህርትና የስብከት ዘዴ፣ በአፍሪካ፤ በግብጽ፣ በኬንያና በአውሮፓ 11 ከተሞች መምህራንን ልኮ ሐዋርያዊ አገልግሎት መስጠቱን የሥራ አስኪያጁ ዘገባ አመልክቷል፡፡

እንዲሁም ለአብነት ትምህርት ቤቶች ደቀመዛሙርት፣ ለንዋየ ቅድሳትና ለአህጉረ ስብከት ድጋፍ፣ ለቅኔ ትምህርት ማስተዋወቅ፣ በተለያዩ አህጉረ ስብከት ርክክብ ለተደረገባቸው ፕሮጀክቶች ማስፈጸሚያና ገና እየተሠሩ ላሉ ፕሮጀክቶች፣ ለአብያተ ክርስቲያናት በነፃ ለተሠሩ የአሠራር ንድፎች /ዲዛይኖች/ በጠቅላላ ከብር 2 ሚሊዮን 760 ሺሕ 186 በላይ ወጪ መደረጉን አስታውቀዋል፡፡

በቅርሳ ቅርስ ምዝገባና ጥበቃ በኩልም በበጀት ዓመቱ ብዙ ጥረት መደረጉን በዘገባቸው ያመለከቱት ሥራ አስኪያጁ በቅርሳቅርስ ቀላጤዎች ተሰርቀው የነበሩ መጻሕፍትንና ንዋየ ቅድሳትን ለማስመለስ በተደረገ ጥረት 22 ጥንታውያን መጻሕፍትን፣ 10 የተለያዩ ንዋያተ ቅዱሳትንና ሁለት ጽላቶችን ለማስመለስ መቻሉን አስረድተዋል፡፡

ግምታቸው 223 ሺሕ 780 ብር የሆኑ ባለሥዕል የብራና ተአምረ ኢየሱስ፣ አንድ የብራና ተአምረ ማርያምና አንድ ድርሳነ ሚካኤል መጽሐፍ በፖሊስ ጣቢያ በኤግዚቢት ተይዘው በምርመራ ላይ ስለሆኑ ቅርሶቹ ወደቦታቸው እንዲመለሱም ክትትል እየተደረገ መሆኑን ዘገባው አመልክቷል፡፡

ዋና ሥራ አስኪያጁ የዋናውንና የየአህጉረ ስብከቶቹን የሥራ እንቅስቃሴ በዝርዝር ያቀረቡ ሲሆን በመ ምሪያዎች፣ በድርጅቶችና በ45 አህጉረ ስብከት አሉ ያሏቸውንም ችግሮች ገልጸዋል፡፡

ካጋጠሙ ችግሮች መካከል በጠቅላይ ቤተክህነቱ ያለው የገንዘብ ወጪ ጫና፣ ከየአህጉረ ስብከቱ ለሚዘዋወሩ ሠራተኞች ደሞዝ ከጠቅላይ ቤተክህነት መከፈሉ፣ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ለሚመረቁ ደቀ መዛሙርት የሚመደበው አዲስ በጀትና የተቋማቱ የውስጥ ገቢ አለመፍጠር፣ ከበጀት ውጪ የሚቀርበው የገንዘብ ጥያቄና ከበቂ በላይ ሠራተኞች እያሉ ተጨማሪ ሠራተኞች ያለ ሥራ መመደብና መቅጠር ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡ በተጨማሪም ወደ ውጪ ሀገርና ሀገር ውስጥም ለአገልግሎት የሚመደቡና የሚላኩትም ወጪያቸው ከዚያው እንዲሸፈን አለመደ ረጉ ይገኙበታል፡፡

የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤን የ 27 ዓመት ጉዞን የሚያሳይ ዐውደ ርእይ የቀረበ ሲሆን ዐውደ ርእዩም በቅዱስ ፓትርያርኩና በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ተባርኮ ተከፍቷል፡፡ ዓውደ ርእዩ ከጥቅምት 6-15 ቀን 2002 ዓ.ም ለዘጠኝ ቀናት ለሕዝብ ክፍት ሆኖ እንደሚቆይ ታውቋል፡፡ ዓውደ ርእዩን የተመለከቱት ተሳታፊዎች በሰጡት አስተያየት የቤተክርስቲያኒቱን ታላቅ ጉባኤ የሚያመለክት በመሆኑ ተጨማሪ የመጎብኛ ጊዜያት እንዲሰጡ ጠይቀዋል፡፡

በስብሰባው ማጠናቀቂያ ላይ ከቤተክርስቲያን ሐዋርያዊ አገልግሎት ጎን ለጎን አገልግሎቷን ለማቀላጠፍ በልማቱ ዘርፍ የላቀ አስተዋጽኦ ያበረከቱ ሀገረ ስብከቶችና አብያተ ክርስቲያናት ሽልማት ተበርክቶላቸዋል፡፡ ለተመረጡት አብያተ ክርስቲያናት ሽልማት የሰጡት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ እንደተናገሩት፤ ቤተ ክርስቲያን በልማቱ ዘርፍ በማሳተፍ ለሀገር ዕድገት የበኩሏን አስተዋጽኦ እያደረገች ነው፡፡

ይህንንም አስተዋጽኦ የበለጠ አጠናክራ እንደምትቀጥል ቅዱስነታቸው ተናግረዋል፡፡ በሠሩት የልማት ሥራ ለሽልማት የበቁት አብያተ ክርስቲያናት የተመረጡት ከመላው ሀገሪቱ ሲሆን አህጉረ ስብከቶቹና የሰበካ ጉባኤ አባላቱ ልማቱን የበለጠ አጠናክረው እንዲቀጥሉ ጄኔሬተር፣ የውኃ ¬ምፕና ኮሚፒዩተር መሸለማቸው ታውቋል፡፡

ለሽልማት ከበቁት ውስጥ የባሌ፣ የሰሜን ሸዋ፣ የምሥራቅ ሸዋና የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት ይገኙበታል፡፡

ጉባኤው ሲጠናቀቅም የጉባኤውን ሒደት በቅደም ተከተል እንዲካሔድ የተሰየመው የቃለ ጉባኤ አርቃቂ ኮሚቴ ባለ 26 ነጥብ ያለው የጋራ የአቋም መግለጫና የውሳኔ ሐሳብ አቅርቧል፡፡

ኮሚቴው ባቀረበው የአቋም መግለጫና የውሳኔ ሐሳብ እንዳመለከተው ቅዱስነታቸው በጉባኤው መክፈቻ ላይ የሰጡት የሥራ መመሪያና በተለይ በሀገራችን ሊከናወን ስለሚገባው ልማታዊ ሥራ፣ ለዚህ ተግባራዊነትም ሊኖር ስለሚገባው ሰላም አስመልክቶ ያስተላለፉት መልእክት ጉባኤው በአድናቆትና ከልብ እንደተቀበለውና ለተግባራዊነቱም እንደሚሠራ ገልጸዋል፡፡

ቅዱስነታቸው በተገኙበት ከየካቲት 9-10 ቀን 2001 ዓ.ም በመንበረ ፓትርያርክ የስብከተ ወንጌል አስተባባሪነት የተካሔደው ዓውደ ጥናት ጠቃሚ ትምህርት የተገኘበት፣ ነፃና ግልጽ በሆነ መንገድ ውይይት የተደረገበትና ተሳታፊዎቹን የበለጠ ለሥራ ያተጋ በመሆኑ ሊበረታታ የሚገባው ጉዳይ መሆኑን የአቋም መግለጫው አመልክቶ መምሪያው በ2002 ዓ.ም ያቀረበው ዕቅድ ተግባራዊ እንዲሆን ጉባኤው መጠየቁን አመልክቷል፡፡

ከጣና ቂርቆስ ገዳም ወደ ፈረንሳይ ተወስዶ በሪስ ሙዚየም ለብዙ ዓመታት የቆየው ቅዱስ መስቀል በቅዱስ ፓትርያርኩ ጥረት ግንቦት 28 ቀን 2001 ዓ.ም መመለሱን ጉባኤው አድንቆና ምስጋና አቅርቦ በቀጣይም በባዕድ ሀገር የሚገኙ ቅርሶችን ወደ ሀገር ቤት ለማስመለስ የሚደረገው ጥረት እንዲጠናከር ጠይቋል፡፡

በአንዳንድ አህጉረ ስብከት ያለው የአብነት ትምህርት ቤት መዳከም ምክንያቱ የአብነት ትምህርት ቤቶች በብዛት የሚገኙት በሰሜኑ የሀገራችን ክፍል መሆኑን የጠቆመው የአቋም መግለጫው ለነዚህም በቂ በጀት አለመመደቡ ይልቁንም በአብዛኛው አህጉረ ስብከት ትምህርት ቤቶች አለመኖራቸው ባሉበትም ቢሆን የሚ ሰጠው ትምህርት ወቅታዊና ዘመናው በሆነ መልኩ ሊካሔድ አለመቻሉን ጉባኤው ግንዛቤ መውሰዱን አመል ክቷል፡፡

ለዚህም በምክንያት የሚጠቀሰው ትምህርትና ማሠልጠኛ መምሪያ በበቂ የሰውና የገንዘብ ኃይል ያልተደራጀ መሆኑ ግንዛቤ መያዙን ኮሚቴው አመልክቶ፤ በዚህ መሠረታዊ በሆነ የቤተክርስቲያን ጉዳይ ላይ ቅዱስ ሲኖዶስ ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ ጉባኤው ማሳሰቡን አስረድቷል፡፡

የነገይቱን ቤተክርስቲያን የሚረከቡና ዛሬም የቤተክርስቲያን ውበት የሆኑት የሰንበት ትምህርት ቤቶች ወጣቶችን በመንከባከብ፣ በማስተማርና ከጠላት ወረራ እንደጠበቁ ለማድረግ፣ ከአባቶች የተማሩትን ንጹሕ ትምህርት ለፍሬ እንዲያበቁ በየአጥቢያ ቤተክርስቲያኑ የሚገኙትን ሰንበት ትምህርት ቤቶች ሁሉ ለማስተማር ያሉትን እያጠናከርን ባልተቋቋመባቸው አብያተ ክርስቲያናትም ለማቋቋም ጥረቱ እንደሚቀጥል የአቋም መግለጫው አመልክቷል፡፡

በበጀት ዓመቱም በተከናወኑ የልማት ሥራዎች በማኅበረ ቅዱሳን በኩል በየአህጉረ ስብከቱ በሚገኙ ወረዳዎችና አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ለልማት ሥራ የሚውል የገንዘብ ድጋፍ መደረጉን በጥንታዊ ትምህርት ቤቶችና በሐዋርያዊ አገልግሎት ተዛማጅ ሥራዎች እንደተከናወኑ ከዘገባው መገንዘቡን በአቋም መግለጫና የውሳኔ ሐሳብ ተጠቁሟል፡፡

በመሆኑም ማኅበረ ቅዱሳን ለቤተ ክርስቲያን ባደረገው እገዛ ጉባኤው እያመሰገነ ወደፊትም ማእከላዊ አሠራርን በጠበቀ መልኩ ማኅበሩ እገዛውን እንዲቀጥል ጉባኤው ማሳሰቡን መግለጫው አስረድቷል፡፡

ኮሚቴው ባቀረበው ባለ 26 ነጥብ የአቋም መግለጫ ሕጋዊ ባልሆኑና ባልተፈቀደላቸው ሰባክያን በየመንደሩም ሆነ በየአብያተ ክርስቲያናቱ የሚካሔዱ ስብከቶች ማዕከላዊ አሠራርን ያልተከተሉ መሆናቸውን፣ በውጪው ዓለም ባለው መለያየት ጉባኤው እንደሚያዝንና በተለይ በሰሜን ምዕራብና ካሊፎርኒያ ሀገረ ስብከት የቀረበው ዘገባ አባቶችን ለማቀራረብ እየተደረገ ያለውን ጥረት እንደሚያደንቁና ጉባኤውም ሰላም እንዲገኝ ሙሉ ድጋፍ እንዳለው በአቋም መግለጫው ተገልጿል፡፡

ማኅበሩ የደብረ ጽጌ ገዳም የአብነት ትምህርት ቤትን በ1 ነጥብ 2 ሚሊዮን ብር ለማደስና ለማስፋፋት ስምምነት ተፈራረመ

በሰሜን ሸዋ ሰላሌ ፍቺ ሀገረ ስብከት የሚገኘው ደብር ቅዱስ ደብረ ጽጌ ማርያም አንድነት ገዳም የአብነት ትምህርት ቤትን ለማጠናከር በማኅበረ ቅዱሳንና በሀገር ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ የአንድ ነጥብ ሁለት ሚሊዮን ብር የፕሮጀክት ስምምነት ተፈራረመ፡፡
ጥቅምት 1 ቀን 2002 ዓ.ም ወደ ስፈራው በተደረገው ሐዋርያዊ ጉዞ ወቅት በማኅበረ ቅዱሳን የፍቺ ማዕከልና የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቆስጦስ የተከናወነው ይኸው የፕሮጀክት ስምምነት አንድ ነጥብ ሁለት ሚሊዮን ብር የሚፈጅ ሲሆን፤ ፕሮጀክቱ ከ3-4 ዓመታት ባለው ጊዜ ውስጥ ይጠናቀቃል፡፡

በፊርማ ሥነ ሥርዓቱ ወቅት በማኅበረ ቅዱሳን የማኅበራዊ አገልግሎት ልማት ዋና ክፍል የቅስቀሳና ገቢ አሰባሰብ ሓላፊ ወ/ሮ ዓለም ፀሐይ መሠረት እንደገለጹት፤ ይኸው የስምምነት ሰነድ የተዘጋጀው ማኅበሩ በነዚህ ዓመታት በአቅም እጥረትና በእርጅና ምክንያት ሳይታደስ በመፈራረስ ላይ የሚገኘውን የአብነት ትምህርት ቤት ለማጠናከር፣ ሦስት አዲስ ቤት ለመገንባት እና ሰባት የጥገና ማስፋፋት ለማካሄድ ነው፡፡

የፕሮጀክቱ አጠቃላይ ወጪ የማኅበሩን የሞያ አገልግሎት እንደማያካትት የገለጹት ወ/ሮ ዓለምፀሐይ፤ እግዚአብሔር ፈቅዶ ፕሮጀክቱን በወቅቱ ለማጠናቀቅ ጥረት እንደሚደረግ አስታወቀዋል፡፡

የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቆስጦስ በዚህ ወቅት እንደ ተናገሩት የቤተክርስቲያኒቱ የነገ ተስፋ የሚፈሩበት ይህ የአብነት ት/ቤት ፈርሶ ቢቀር ከፍተኛ ሐዘን ይሰማቸው እንደነበር ጠቅሰው፤ ማኅበሩ ይህን በማሰብ ያከናወነው ተግባር የሚያሰመሰግነው መሆኑን ተናግርዋል፡፡

ለፕሮጀክቱ ተግባራዊነት በዋናነት በሓላፊነት እንደሚንቀሳቀሱና ለግንባታውም ባላቸው አቅም በገንዘብ እንደሚራዱ የጠቀሱት ብፁዕነታቸው፤ ምእመናን በሥራው እገዛ እንዲያደርጉ ጠይቀዋል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ወደ ማኅበረ ምእመናን እያደገ እንደሚገኝም ገልጸዋል ከፕሮጀክቱ ስምምነቱ በተጨማሪም ማኅበሩ ከምእመናን ያሰባሰበውን 13 ሺሕ 200 ብር ግምት ያላቸው 108 መንፈሳ ውያን መጻሕፍት፣ መጽሔትና ጋዜጦች ለገዳሙ  የአብነት ት/ቤት በስ ጦታ አበርክተዋል፡፡

ከዛሬ 50 ዓመታት በፊት የተቋቋሙ ይኸው የአብነት ት/ቤት የተመሠረተው በብፁዕ አቡነ ባስልዮስ መሆኑ በፕሮጀክት ስምምነቱ ወቅት ተጠቁሟል፡፡

በእንግድነት የተገኙት የታዕካ ነገሥት ባዕታ ለማርያም ገዳም እና የመንበረ መንግሥት ቅዱስ ገብርኤል የበላይ ጠባቂ ብፁዕ አቡነ ስምኦን እና የመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም የበላይ ጠባቂ ብፁዕ አቡነ ኤርምያስ በበኩላቸው ባስተላለፉት መልእክት፣ ነገ የቅድስት ቤተክርስቲያንን አገልጋይ መፍለቂያ የሚሆኑት የአብነት ት/ቤቶ ችን ለማጠናከር እየተደረገ ያለው ጥረት የሚበረታታ መሆኑን ጠቅሰው፤ ለፕሮጀክቱ ማስፈጸሚያ እነርሱም በየግላቸው የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እንደሚያደረጉ ቃል ገብተዋል፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጸሐፊ አቶ ዳንኤል ተስፋዬ በበኩላቸው ማኅበሩ ገዳማትና አድባራትን በመደገፍ እንዲሁም የአብነት ት/ቤቶችን ከማጠናከር በተጨማሪ በርካታ ማኅበራዊና መንፈሳዊ አገልግሎቶችን እየሰጠ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡

በአሁኑ ወቅት በርካታ የአብነት ት/ቤቶች እየተዳከሙ እንደሚገኙ የገለጹት ዋና ጸሐፊው ይህን ችግር ለመቅረፍ ማኅበሩ በጎ አድራጊ ግለሰቦችንና ማኅበራትን እንዲሁም ምእመናንን በማስተባበር ፕሮጀክት ቀርጾ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን አብራርተዋል፡፡

በዚህ መንፈሳዊ ጉብኝት እና የፕሮጀክት ስምምነት ወቅት ከ300 በላይ የበጎ አድራጊ ግለሰቦች እና የመንፈሳዊ ማኅበራት ተወካዮች የተገኙ ሲሆን የአብነት ት/ቤቶችን ለማጠናከር በሚደረገው ጥረት ውስጥ ከማኅበረ ቅዱሳን ጎን እንደሚቆሙ ቃል ገብተዋል፡፡

የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ መጠናከር የቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ አገልግሎት ለማስፋፋት መሠረት ነው

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስተያንን ሐዋርያዊ አገልግሎት ለማስፋፋት፣ አገልጋዮቿን መዝግባ ይዛ ሥምሪት እና ምደባ ለመስጠት፣ ችሎታቸውንና ኑሮአቸውን ለማሻሻል፣ ምእመናንን ለማብዛትና በመንፈሳዊ እውቀት ጎልምሰው፣ በምግባርና በሃይማኖት ጸንተው እንዲኖሩ ለማድረግ፣ የቤተ ክርስቲያንን አስተዳደር ለማሻሻልና በሚያስፈልጋት ማንኛውም ጉዳይ ራሷን ለማስቻል ከአጥቢያ ቤተ ክርስቲያን ጀምሮ እስከ መንበረ ፓትርያርክ ድረስ በየደረጃው የሚቋቋም የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ መዋቅርና አሠራር በቃለ ዓዋዲው መሠረት ዘርግታ ትገኛለች፡፡
የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤዎች በሕዝብ በሚመረጡ ካህናት፣ ምእመናን እና የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች ተሳትፎ የቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ አገልግሎት ለማስፋፋትና አስፈላጊ የሆነውን አቅም ለማጐልበት የሚመክርባቸው፣ የሥራ ክንዋኔዎችና ችግሮች እየቀረቡ የሚገመገሙባቸውና ልምዶች የሚወስዱባቸው፣ ቀጣይ አቅጣጫዎችም እግዚአብሔር ቢፈቅድ በሚል የሚታይባቸው በመሆናቸው፤ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ መዋቅር ለቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ አገልግሎት መስፋፋት ወሳኝነት ያለው ነው፡፡

ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ብቻ ሳይሆን በዓለም ላይ በሚገኙ በአኀት አብያተ ክርስቲያናትም በእንግሊዘኛው አጠራር /ሪሽ ካውንስል/ በሚል ስያሜ እየተሠራበት የሚገኝ ዘመናዊ የቤተ ክርስቲያን አስተዳደራዊ መዋቅር ነው፡፡

የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ /ሪሽ ካውንስል/ መዋቅርና አሠራር ሀገር አቀፍና ዓለም አቀፍ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ለውጦች በምእመናን ላይ የሚያስከትሉትን ተጽዕኖና መልካም አጋጣሚ ባገናዘበ ሁኔታ የቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ አገልግሎት ማስፋፋትና ለዚህም የሚያስፈልገውን ዐቅም መፍጠርና ማጠናከር፣ የምእመናን ችግር መፍቻ እንዲሆኑ ለማድረግ አብያተ ክርስቲያናት፡- አካባቢያዊ እና የምእመናንን አኗኗር ሁኔታዎች እንዲሁም ቤተ ክርስቲያን ማድረግ የሚገባትን ዘመኑን የዋጀ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ /ሪሽ ካውንስል/ መዋቅርና አሠራር ለመዘርጋት ተጨባጭና ነባራዊ ሁኔታዎችን የተከተሉ የሕግና የመዋቅር ማሻሻያዎችን ያደርጋሉ፡፡ የአሠራር ስልቶችን በየጊዜው ያዳብራሉ፡፡

ከዚህ አኳያም በ1991 ዓ.ም ለሦስተኛ ጊዜ ተሻሽሎ በሚገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰበካ መንፈሳዊ ደንብ /ቃለ ዓዋዲ/ አንቀጽ 61  /2/ /ሀ/ ላይ የሰበካ ጉባኤ የሚኖረውን የምእመናን ድርሻ በተመለከተ፡- «የሰበካ ምእመናን በገንዘብ አስተዋጽኦ፣ በአስተዳደር፣ በትምህርት፣ በልማትና በማኅበራዊ ኑሮ አገልግሎት በጠቅላላው በሀብት፣ በዕውቀትና በጉልበት በመረዳት በሰበካው ልዩ ልዩ የክፍል ሥራዎች ውስጥ በመሳተፍ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ማገልገል ክርስቲያናዊ ግዴታቸው ነው፡፡» በማለት በተደነገገው መሠረት ምእመናን ለቤተ ክርስቲያናቸው የሚጠበቅባቸውን አገልግሎት ሲሰጡ ለሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ዓላማ መሳካት ትልቅ ድርሻ ያለው ነው፡፡

በቤተ ክርስቲያናችን ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ደንብ /ቃለ ዓዋዲ/ መሠረት በአጥቢያ ቤተ ክርስቲያን የሚከተሉት ክፍሎች ይኖራሉ፡-

ሀ/ የስብከተ ወንጌል ክፍል
ለ/ የመንፈሳዊ ትምህርት ክፍል
ሐ/ የካህናት አገልግሎት ክፍል
መ/ የሰንበት ት/ቤት ክፍል
ሠ/ የእቅድና ልማት ክፍል
ረ/ የምግባረ ሠናይ /በጐ አድራገት/ ክፍል
ሰ/ የሕግና ሥነ ሥርዓት ክፍል
ሸ/ የንብረት፣ የዕቃ ግምጃ ቤትና የታሪካዊ ቅርስ ክፍል
ቀ/ የሒሳብ ክፍል
በ/ የገንዘብ ቤት
ተ/ የቁጥጥር ክፍል
ቸ/ የሕንፃ ሥራ፣ እድሳትና ጥገና ክፍል
ኀ/ የስታቲስቲክስ ክፍል

በሚል የተዋቀሩ የሥራ ክፍሎች ያሉት ሆኖ ምእመናን በችሎታቸው በቤተ ክርስቲያን አስተዳደር መሳተፍ እንዲችሉ የሚያደርግ ሲሆን ዳር ቁመን የምንመለከተው ወይም እገሌ ይሠራዋል፤ በሚል ልንሸሸው የማይገባ፣ ተሳታፊ በመሆን በረከት የምናገኝበት እና የቤተ ክርስቲያን ችግር የሚቀረፍበት መዋቅር ነው፡፡

በመሆኑም በሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ደንብ መሠረት የሚጠበቅብንን  የድርሻችንን ካልተወጣንና ለቤተ ክርስቲያን የሚጠቅመውን በወቅቱ ካላደረግን ደንቡና መዋቅሩ ብቻውን ትርጉም ሊኖረው ስለማይችል በተሰጠን ጸጋ ልናገለግል ይገባል፡፡ እግዚአብሔርም ከእኛ ብዙ ይጠብቃል፡፡ የተቀበልነው መክሊት ነውና በተሰጠን መጠን ይፈለግብናል /ማቴ. 25-14-30/፡፡

በጉባኤ ደረጃ ያለውን ኃላፊነት ስንመለከት የአጥቢያ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ፤ የአጥቢያው ካህናት፣ ምእመናን እና የሰንበት ት/ቤት ተማሪዎች የሚሳተፉበት በዓመት ሁለት ጊዜ የሚካሄድ ጠቅላላ ጉባኤ ያለው ሲሆን፤ የወረዳ፣ የሀገረ ስብከት እና የመንበረ ¬ፓትርያርክ ሰበካ ጉባኤዎችም በየደረጃቸው በዓመት አንድ ጊዜ በመሰብሰብ አፈጻጸማቸውን በማቅረብ ውይይት የሚያደርጉባቸው የሰበካ መንፈሳዊ ጠቅላላ ጉባኤዎች የሏቸው ስለሆነ፤ እኒህ በተለያየ ደረጃ የሚደረጉት ጠቅላላ ጉባኤዎች የበለጠ ውጤታማ እንዲሆኑ ለማድረግ ቅድመ ዝግጅት እና ከጉባኤዎቹ በኋላም ቢሆን ክትትል ማድረግን የሚሹ ናቸው፡፡

በዚህም መሠረት የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤዎችን በማጠናከር የቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ አገልግሎት ለማስፋፋት ከቀደምት ተሞክሮዎች አንፃር

ምእመናን፣ የቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ አገልግሎት ለማገዝ በሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ድርሻ ስላላቸው፡- በሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ በመምረጥና በመመረጥ ቢሳተፉና የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤያቸውን በገንዘባቸው፤ በሙያቸው እና በጉልበታቸው ቢያገለግሉና ሌሎች ምዕመናንን የቤተ ክርስተያንን ችግር ለመቅረፍ የሰበካ ጉባኤ ተሳትፎ ወሳኝ እንደሆነ አጽንኦት ቢሰጡ፤

በቃለ ዓዋዲው የተገለጸው እንደተጠበቀ ሆኖ በየደረጃው ለሚገኙ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤዎች ችግር ፈቺ  የሆነ፣ ዘመኑን የሚዋጅ ስትራተጂክ እቅድ እንዲወጣላቸው እና ከጉባኤዎቹ ስብሰባ በፊትና በኋላ አፈጻጸሙ ጽኑ ክትትል የሚደረግበት ሁኔታ ቢጠናከር፤

የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤያት የእስካሁን አፈጻጸም ምን እንደሚመስል እና በቀጣይ መሻሻል የሚገባቸው አሠራሮች ምን እንደሆኑ የሚያወያዩ ጥናት በየደረጃው እንዲቀርብ ቢደረግ፤

የሰበካ መንፈሳዊ አጠቃላይ ጉባኤያት የበለጠ ውጤታማ እንዲሆኑ ለማድረግ ጉባኤዎቹ ሪፖርቶች ማዳመጥ ብቻ ሳይሆን ችግር ፈቺ በሆኑ ጉዳዮች ላይ የጠነከረ ውይይት ሊያደርጉ ስለሚችሉበት ሁኔታ በሁሉም ደረጃዎች ወጥነት እንዲኖረው ቢደረግ፤

በሰበካ መንፈሳዊ ጠቅላላ ጉባያት የሚወሰኑ ጉዳዮች ጊዜ በማይወሰድ ሁኔታ ታች በየደረጃው ለሚገኙ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤያት ለአፈጻጸም እና ለግንዛቤ እንዲደርሱ አሠራሩ የተጠናከረ እንዲሆን ቢደረግ፤ እና በአንዳንድ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤዎች የሚፈጠሩ አለመግባባቶችን አጣርቶ የመፍትሔ እና የውሳኔ ሐሳብ የሚያቀርብ ትጉህ እና ለችግሮች ገለልተኛ የሆነ ምእመናን የሚሳተፉበት አሠራር መዋቅራዊ እንዲሆን ቢደረግ፤

የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤን ዓላማና ተግባር ለማሳካት አስተዋጽኦ ስለሚኖረው፤ ያልፈጸምነውን አጉልተን በማየት፣ ቅድመ ዝግጅት እና ተሳትፎ በማድረግ የሚጠበቅብንን ልንወጣ ይገባል፡

እስከ ሞት ድረስ የታመንህ ሁን – ራዕ. 2.10

በዲ. ኤፍሬም ውበት

 
 
ክርስትና በእምነት እያደጉ እና እየጠነከሩ ዘወትር የሚጎለብቱበት ሕይወት ነው፡፡ በመሆኑም አንድ ክርስቲያን ከትናንት ዛሬ ከአምና ዘንድሮ አድጎና ጠንክሮ መገኘት አለበት፡፡ «ንቁ በሃይማኖት ቁሙ ጎልምሱ ጠንክሩ» እንደተባለ በጊዜውም /በተመቸ ጊዜ/ ያለጊዜውም/ባልተመቸ ጊዜም/ በእምነት ጸንቶ ለመገኘትና እስከ ሞት ድረስ ለመታመን የግድ በእምነት አድጎና ጠንክሮ መገኘት ያስፈልጋል፡፡ /1ቆሮ.6.13ጠ14/፡፡ እምነትን በምግባርና በትሩፋት ለመግለጽም ራስን በመካድ ፈቃደ ሥጋን ለፈቃደ ነፍስ ማስገዛት ይገባል፡፡ ለዚህም መከራን እየታገሱ ራስን ከዓለም መለየት ይገባል፡፡ በዚህ ዓይነት ፈቃደ ሥጋውን ለፈቃደ ነፍሱ በማስገዛት በእምነቱ የጠነከረ ሰው ከማናቸውም ነገር ይልቅ መንግሥቱንና ጽድቁን ያስቀድማል፡፡ /ማቴ.6.13/፡፡ ይህም ማለት ሃይማኖትን ከምግባር አዋሕዶ ልጅነቱን አጽንቶ ጽድቅ የሚገኝበትን ሀገር መንግሥተ ሰማያትን ተስፋ አድርጎ ይኖራል ማለት ነው፡፡ በዚህም የመንፈስን ፍሬ የሚያፈራ በአፀደ ቤተ ክርስቲያን የተተከለ የሃይማኖት ተክል ይሆናል፡፡ /ገላ.5:22/፡፡ ተክልነቱም በውኃ ፈሳሾች ዳር እንደተተከለች ፍሬዋን በየጊዜው እንደምትሰጥ፣ ቅጠልዋም እንደማይረግፍ ዛፍ ነው፡፡ እንዲህ ዓይነቱም ሰው በክፋዎች ምክር አይሄድም፡፡ በኃጢአተኞችም መንገድ አይቆምም፡፡ በዋዘኞችም ወንበር አይቀመጥም፤ ነገር ግን በእግዚአብሔር ሕግ ደስ ይለዋል፡፡ ሕጉንም በቀንና በሌሊት ያስባል፡፡ /መዝ.1.3/፡፡

 

ቅዱስ ጳዉሎስ የተሰሎንቄ ምእመናን በእምነት አድገውና ጠንክረው በማየቱ «በጸሎታችን ጊዜ ስለ እናንተ ስናስብ የእምነታችሁን ሥራ የፍቅራችሁንም ድካም በጌታችንም በኢየሱስ ክርስቶስ ያለውን የተስፋችሁን መጽናት በአምላካችንና በአባታችን ፊት ሳናቋርጥ እያሰብን እግዚአብሔርን ሁልጊዜ በሁላችሁ ምክንያት እናመሰግናለን፡፡» በማለት ስለእነርሱ እግዚአብሔርን አመስግኗል፡፡ /1ተሰ.1.2ጠ3/፡፡ ከጥንት ጀምሮ በእምነታቸው ጠንካሮች የነበሩ ሰዎች በጉዟቸው ሁሉ እግዚአብሔርን ደስ አሰኝተዋል፡፡ እግዚአብሔርም ደስ የተሰኘባቸው በእምነታቸው ጸንተው በጎ ሥራ በመሥራታቸውና ዓለምን ድል በማድረጋቸው ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳዉሎስ በዕብራውያን መልእክቱ እንደዘረዘረው፡

 

•    አቤል ከቃየል ይልቅ የሚበልጥ መሥዋዕትን ያቀረበው፣
•    አብርሃም ከዘመዶቹ ተለይቶ ከሀገሩ የወጣው፤ አንድ ልጁን ይስሐቅንም ለመሠዋት ፈቀደኛ የሆነው፣
•    ሙሴ የግብጽን ብዙ ገንዘብ የናቀውና ከወገኖቹ ጋር መከራ መቀበልን የመረጠው፤ የፈርኦን የልጅ ልጅ እንዳይባል እምቢ ያለው፣
•    የኢያሪኮ ግንብ በእስራኤላውያን ጩኸት የፈረሰው፣
•    ጌዴዎንና ባርቅ፣ሶምሶንና ዮፍታሔ ጠላቶቻቸውን ድል ያደረጉት፣
•    ብላቴናው ዳዊት ኃይለኛውን ጎልያድን ያሸነፈው፣
•    ሠለስቱ ደቂቅ ወደ እቶነ እሳት ቢጣሉም ከመቃጠል የዳኑት በእምነት ነው፡፡ /ዕብ.11.1ጠ4/፡፡

 

በአዲስ ኪዳንም ቅዱሳን ሐዋርያት ሁሉን ትተው እስከ መጨረሻው የተከተሉት በእምነት ነው፡፡ /ማቴ.19.27/ ከእነርሱም ሌላ በሰው ዘንድ ያልተጠበቁ፣ በእርሱ ዘንድ ግን የታወቁ ጥቂት ሰዎች የእምነታቸው ጽኑነት ተመስክሮላቸዋል፡፡ ለምሳሌ ከነናዊቷ ሴት «አንቺ ሴት እምነትሽ ታላቅ ነው እንደ ወደድሽ ይሁንልሽ» ተብላለች፡፡ /ማቴ. 15.28/፡፡ በእምነት የጸኑ ሰዎች የቤተክርስቲያንን ሥርዓት፣ ትውፊት ለመጠበቅ መልካሙን ገድል ይጋደላሉ፡፡ /2ጢሞ.4.7/፡፡

አንድ ክርስቲያን በክርስትና ሕይወት እስከ ሞት ድረስ ታምኖ የመንግሥቱ ወራሽ ለመሆን ሊያከናውናቸው ከሚገቡ መንፈሳዊ ተግባራት ጥቂቶችን እንመለከታለን፡፡

 

1. የእግዚአብሔር ስጦታዎች ሁሉ ለበጎ መሆናቸውን ማመን

 

በማናቸውም ጊዜ እግዚአብሔር ሁሉን የሚሰጥ አምላከ መሆኑን መዘንጋት የለብንም፡፡ ሌላው ቀርቶ ለእኛ ክፉ የሚመስሉን ነገሮችን እንኳን ለበጎ መሆናቸው ማመን አለብን፡፡ /ሮሜ.8.28/፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሔር ክፉውን ወደ በጎ ሊለውጥ የሚችል ኃያል አምላክ ነውና፡፡ ብላቴናው ዮሴፍ ባሪያ አድርገው የሸጡትን ወንድሞቹን «እናንተ ክፉ ነገር አሰባችሁብኝ እግዚአብሔር ግን ዛሬ እንደ ሆነው ብዙ ሕዝብ እንዲድን ለማድረግ ለመልካም አሰበው፡፡» ያላቸው ለዚህ ነው፡፡ /ዘፍ.50.20/፡፡ አበ ብዙኃን አብርሃም እግዚአብሔር «ልጅህን ሠዋልኝ» ያለው ለበጎ እንደሆነ ያውቅ ነበር፡፡ ማወቅም ብቻ ሳይሆን እንደተባለው ልጁን ቢሠዋ እንኳን ከሞት አስነሥቶ በእርሱ በኩል ዘሩን እንደሚያበዛለት ያምን ነበር፡፡ /ዕብ.11.17/፡፡ ኢዮብም ነገር ሁሉ ለበጎ እንደሆነ አውቆ «እግዚአብሔር ሰጠ እግዚአብሔርም ነሣ የእግዚአብሔር ስም የተባረከ ይሁን» ብሏል፡፡ /ኢዮ.1.21/፡፡

 

2. የእግዚአብሔርን ቃል ኪዳኖች ማመን

 

ብዙ ሰዎች እግዚአብሔር የሰጣቸው ተስፋ ደርሶ ቃሉ የሚፈፀም አይመስላቸውም፡፡ ነገር ግን የእግዚአብሔር ቃል ያለጥርጥር ይፈጸማል፡፡ ለአዳምና ለሔዋን የተሰጠው ተስፋ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ቤዛነት ተፈጽሟል፡፡ /ዘፍ.3.15/፡፡ ለኤልያስ የተሰጠው ተስፋ ምንድን ነው) የተሰጠው ተስፋ በሰራፕታዊቷ ሴት መጋቢነት ሲፈጸም ታይቷል፡፡ እንዲሁም በነቢዩ በኢዩኤል አንደበት የተነገረው ተስፋ የበዓለ ሃምሣ ዕለት ለቅዱሳን ሐዋርያት በመሰጠቱ ተፈጽሟል፡፡ /ኢዩ.2.28፤ ሐዋ.2.16/፡፡ በዚህ ዓይነት እግዚአብሔር ለሕዝቡ የገባውን ቃል ኪዳን እንደማይሽርና ከአፉ የወጣውን ቃል እንደማይለውጥ ማመን ይገባል፡፡/መዝ.88.34/፡፡ በቤተ ክርስቲያን በምንሰበሰብበት ጊዜ ሁለት ወይም ሦስት በስሜ በሚሰበሰቡት በዚያ እኔ በመካከላቸው እሆናለሁ ባለው መሠረት በመካከላችን እንደሚገኝ የታመነ ነው፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ቤተ ክርስቲያን ከውስጥም ሆነ ከውጭ መከራ በሚበዛባት ጊዜ መከራ የሚያስነሣባትና የሚያጸናባት ዲያብሎስ መሆኑን አውቀን «የገሃነም ደጆችም አይችሉአትም» በሚለው ቃል ኪዳን መጽናት ይገባል፡፡ /ማቴ.16.18/፡፡ መናፍቃን ከእውነት መንገድ ለማውጣት በሚከራከሩን ጊዜም «ወደረኞቻችሁ ሁሉ ሊቃወሙና ሊከራከሩ የማይችሉትን አፍና ጥበብ እሰጣችኋለሁ»የሚለውን ቃል ኪዳን በማሰብ መታመን ያስፈልጋል /ሉቃ.21.15/፡፡

 

3. በችግር ጊዜ የእግዚአብሔርን ቸርነትና ፈቃድ ተስፋ ማድረግ

 

በመንፈሳዊ ጎዳና ስንጓዝ በየአቅጣጫው የሚከበንን መከራ አይተን ተስፋ መቁረጥ ሳይሆን ወደ እግዚአብሔር ተመልክተን አዳኝነቱን ተስፋ ማድረግ አለብን፡፡ ሊቀ ነቢያት ሙሴ ወገኖቹ እስራኤል ቀይ ባሕርን ከኋላ ደግሞ የፈርኦንን ሠራዊት ተመልክተው ተስፋ በቆረጡ ጊዜ «ቁሙ፣ ዛሬ ለእናንተ የሚያደርጋትን የእግዚአብሔርን ማዳን እዩ፡፡» ያላቸው ለዚህ ነው፡፡ /ዘዳ.14.13ጠ14/፡፡

ብላቴናው ዳዊት የተመለከተው በአካሉ ግዙፍ ወደሆነው ወደ ጎልያድ ሳይሆን ወደ እግዚአብሔር አዳኝነት ነው፡፡ /1ሳሙ.17.46/፡፡በአጠቃላይ ዓለም ድብልቅልቅ ቢል ተስፋ መቁረጥ አይገባም፡፡ ምክንያቱም «እግዚአብሔር በወጀብና በዓውሎ ነፋስ መካከል መንገድ አለውና»/ናሆ.1.3/፡፡

 

4. የቅዱሳንን ገድል ማሰብ

 

ቅዱሳን አንድ ጊዜ ስለተሰጣቸው ሃይማኖት እሰከ መጨረሻው ተጋድለዋል፡፡ /2ጢሞ.4.7/፡፡ በሰይፍ ተመትተዋል፣ በእሳት ተቃጥለዋል፣ ለአናብስት ተሰጥተዋል፣ ወደ ጥልቅ ባሕር ተጥለዋል፣ ይህም የሚያሳየን የእምነታቸውን ጥንካሬ ነው፡፡ በመሆኑም የቅዱሳንን ገድል በምናስብበት ጊዜ ከእነርሱ የምንማረው እምነታቸውን፣ ሥርዓታቸውንና ትውፊታቸውን ለመጠበቅ መጽናታቸውን ነው፡፡ መማርም ብቻ ሳይሆን በተሰጣቸው ቃል ኪዳንም እንጠቀማለን፡፡ እስራኤል ዘሥጋ «እናንተ ጽድቅን የምተከተሉ እግዚአብሔርንም የምትሹ ስሙኝጠ ከእርሱ የተቆረጣችሁበትን ድንጋይ ከእርሱም የተቆፈራችሁበትን ጉድጓድ ተመልከቱ፣ ወደ አባታችሁ ወደ አብርሃም ወደ ወለደቻችሁም ወደ ሣራ ተመልከቱ፡፡ አንድ ብቻውን በሆነ ጊዜ ጠራሁት፣ ባረኩትም፣ አበዛሁትም፡፡» የተባለለት ለዚህ ነው፡፡ /ኢሳ.51.1/፡፡

ቅዱስ ጳውሎስም «የእግዚአብሔርን ቃል የተናገሩአችሁን ዋኖቻችሁን አስቡ የኑሮአቸውንም ፍሬ እየተመለከታችሁ በእምነታቸው ምሰሉአቸው» ብሏል /ዕብ.13.7/፡፡ በአጠቃላይ እግዚአብሔር ከእኛ ጋር መሆኑንና ሥራችንን ሁሉ እንደሚከናውንልን፣ ከሁሉም በላይ እንደሚወደን ማመን ያስፈልጋል፡፡ /ዘፍ.15.21፤1.22፤ መሳ.16.3/፡፡ ምክንያቱም አንድ ልጁን እንኳን አልከለከለንምና /ዮሐ.3.16/፡፡ የእግዚአብሔር ፍቅር በእኛ ዘንድ ተገለጠ፣ በእርሱም በኩል በሕይወት እንኖር ዘንድ እግዚአብሔር አንድ ልጁን ወደ ዓለም ልኮታልና፡፡ /1ዮሐ.4.9/፡፡ እርሱም በትምህርቱ «ከእንግዲሀ ወዲህ ባሮች አልላችሁም ወደጆች ግን ብያችኋለሁ» ብሎናልና፡፡ /ዮሐ.15.15/፡፡ በመጨረሻም ስለማናቸውም ነገር እንደምንጸልይ ሁሉ ስለ እምነታችንም ጽናት ልንጸልይ ይገባል፡፡ እንዲህ ከሆነ እምነታችን ዕለት ዕለት እያደገ እየጠነከረ ይሄዳል፡፡ በአንጻሩ ደግሞ እስከ ሞት ድረስ እንዳንታመን በእምነትና በምግባር እንዳንጸና የሚያደርጉን ፈተናዎች አሉ፡፡ ከእነዚህም ውስጥ ጥቂቶቹ፡

 

1. የራስን ክብር መሻት

 

ብዙ ሰዎች የእግዚአብሔርን ክብር ትተው የራሳቸውን ምድራዊ ክብር ሲፈልጉ እምነታቸው ደክሞባቸዋል፡፡ ዲያብሎስ ከክብሩ የተዋረደው፣ ሄሮድስ ሕፃኑን ኢየሱስ ክርስቶስን ለመግደል ያሳደደው፣ ፈሪሳውያን እርስ በርሳቸው ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ «እነሆ ዓለሙ ሁሉ በኋላው ተከትሎት ሄዷል፡፡» በማለት ይቃወሙት የነበረው የራስን ክብር በመሻት ነው፡፡ /ማቴ.2.17፤ ዮሐ.12.19/፡፡ ይሁን እንጂ ምድራዊ ክብር ፈጥኖ እንደ ሣር ይጠወልጋል፣ እንደ አበባም ይረግፋል፡፡ /ኢሳ.40.6፤1ጴጥ.1.24/፡፡ ስለሆነም እንደ ቅዱስ ጳውሎስ «ነፍሴን/ሰውነቴን/ በእኔ ዘንድ እንደማትከብር እንደ ከንቱ ነገር እቆጥራለሁ» ማለት ይገባል፡፡

 

2. እምነትንና ዕውቀትን መደባለቅ

 

የሰው ልጅ አእምሮው ውሱን፣ ዕውቀቱም የተገደበ ስለሆነ ነገረ ሃይማኖትን ከአቅሙ በላይ ለመተንተን ይከብደዋል፡፡ ስለሆነም የረቀቀውን የእግዚአብሔርን አሠራር ስፋቱንና ጥልቀቱን በሥጋዊ ዕውቀቱ እመረምራለሁ ሲል ከተሳሳተ ሀሳብ ላይ ደርሶ ይሰናከላል፡፡ በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ላይ እንደምናየው በመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን የነበሩት ግኖስቲኮች ከሃይማኖት ተሳስተው የወደቁት፣ ሃይማኖትንና ዕውቀትን በመደባለቅ ለመጓዝ ባደረጉት ሙከራ ነው፡፡ ሥጋዊውን ዓለም ልንመረምር እንችላለን እንጂ የመንፈስ ቅዱስን ሥራ ልንመረምር አንችልም፡፡ በመሆኑም ሊቃውንት በእምነት ተራቅቀው ብዙ የሃይማኖትን ምሥጢር ባወቁ ቁጥር የሚያውቁት ገና አለማወቃቸውን ነው፡፡ ስለሆነም ውሱን የሆነ ዕውቀታችንን በትህትናና በትዕግሥት እግዚአብሔርን ከማገልገል ጋር ልንጠቀምበት ይገባል፡፡

 

3. ክፉ ባልንጀርነት

 

ከመናፍቃን ጋር በመወዳጀት የእነርሱን ስብከትና መዝሙር መስማት እምነትን ያደክማል፡፡ ምክንያቱም የመዝሙሩ መሣሪያና ስሜት ለሥጋዊ ሀሳብና ፈቃድ መጥፎ ጎን መነሣሣት ይፈጥራልና፡፡ ሃይማኖታዊ ሳይሆን ስሜታዊ ያደርጋል፡፡ የዜማው ስልተ አልባ መሆንና ከዘፈን ጋር ተመሳሳይ በመሆኑ ዓለማዊነት ጠባይ የለበትም መንፈሳዊ ነው ለማለት ያዳግታል፡፡ ለዚህም ነው «ክፉ ባልንጀርነት መልካሙን አመል ያጠፋዋል» የተባለው /1ቆሮ.15.33/፡፡ በሃይማኖት በሥርዓት ከማይመስል ጋር ለመመሳሰል መሞከር፣ አብሮ ማደርም ሆነ መዋል መልካሙን እምነት ያጠፋዋል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም በመልእክቱ «በቤታችሁ አትቀበሉት ሰላምም አትበሉት ሰላምም የሚለው ሰው በክፉ ሥራው ይካፈላልና፡፡» ብሏል፡፡ /2ዮሐ.1.10 – 12/፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም «ከማያምን ጋር በማይመች አካሄድ አትጠመዱ፡፡» ብሏል፡፡ ስለሆነም ብርሃን ከጨለማ ጋር ምንም አንድነት ስለሌለው መለየት ያስፈልጋል፡፡ /2ቆሮ. 6.14-16/፡፡

 

4. ክፉ ወሬ

 

ምእመናን ስለ ሃይማኖታቸው መስማት የሚገባቸው ቤተ ክርስቲያናቸው የምትነግራቸውን መሆን አለበት፡፡ ምክንያቱም «ጦር ከፈታው ወሬ የፈታው» እንዲሉ በወሬ የተፈቱ ብዙዎች ናቸውና፡፡ እስራኤል ዘሥጋ ምድረ ርስትን ከመውረስ የደከሙትና በእግዚአብሔር ላይ የነበራቸውም ተስፋ የጠወለገው፣ ዐሥሩ ሰላዮች ያወሩትን እምነት የጎደለው ወሬ እውነት ነው ብለው በመቀበላቸው ነበር፡፡ /ዘኁ.13. 28/፡፡ በአዲስ ኪዳንም ጌታችን ሞትን ድል አድርጎ በተነሣ ጊዜ አይሁድ «ደቀ መዛሙርቱ በሌሊት መጥተው ከመቃብር ሰርቀው ወሰዱት» ብለው አስወርተው ነበር፡፡ ይህም ወሬ መግደላዊት ማርያምን አሳምኗት ስለነበረ ከአንዴም ሦስት ጊዜ ጌታን ከመቃብር ወስደውታል እስከ ማለት ደርሳለች፡፡ /ዮሐ. 20.2-13፤15/፡፡ ጥንትም አዳምና ሔዋን ከእግዚአብሔር የተጣሉት የሰይጣንን ወሬ እውነት ነው ብለው በመቀበላቸው ነበር፡፡ /ዘፍ.3.4/፡፡ ምክንያቱም የሐሰት ወሬ ከዲያብሎስ ነው፤ የሐሰት አባት እርሱ ነውና፡፡ /ዮሐ.8.44/፡፡ በእምነት መድከም በመጀመሪያ ሥርዓትን ትውፊትን ያስንቀናል፡፡ በሃይማኖት ለሚኖር ሰው ይህ ደግሞ አግባብ አይደለም፡፡ እንግዲህ ይህንን ሁሉ አውቀን በጊዜውም አለጊዜውም በሃይማኖት በምግባር ጸንተን ልንገኝ ይገባል፡፡ በእምነታችን እንድንጸና ምክንያት ሳናበዛ እምነታችንን ከሚያዳክሙ እኩይ ተግባራት በመራቅ እምነትን የሚያጠናክሩትን በጎ ተግባራት ሁሉ መያዝ አለብን፡፡ «በዓመፀኞች ስሕተት ተስባችሁ ከራሳችሁ ጽናት እንዳትወድቁ ተጠንቀቁ» እንደተባለ በማንም ሳንወሰድ የቅዱሳን አባቶቻችንን ሃይማኖት ከምግባር አስተባብረን ልንይዝ ይገባናል፡፡ /2ጴጥ.3.17/፡፡

 

5. ሥጋዊ መከራን መፍራት

 

ሥጋዊ መከራን መፍራት እምነትን ያደክማል፡፡ ይህም ለዘለዓለም ሞት አሳልፎ ይሰጣል፡፡ /ራዕ.21.7/፡፡ እግዚአብሔር ግን የፍርሃትን መንፈስ አላሳደረብንም /2ጢሞ.1.7/፡፡ ለሥጋ ፍላጎት መገዛት ማለትም ለዝሙት፣ ለገንዘብና ለሥልጣን ወዘተ መገዛትም እምነትን ያዳክማል፡፡ /1ነገ.11.1፤ ማቴ.19.22፤ ዮሐ.5.4-9፤ ዕብ.4.4፤ 2ጴጥ.2.15፤3ዮሐ.10፤ ራዕ.2.14/፡፡ ምድራዊ ችግርም ሲያዩት የሚያልፍ ስለማይመስል እምነትን ያዳክማል፡፡ ጌዴዎን «ጌታዬ ሆይጠ እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ከሆነ ይህ ነገር ሁሉ ለምን ደረሰብን)» ያለው በምድራዊ ችግር ብዛት እምነቱ ደክሞ ስለነበር ነው፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያትም የማዕበሉን ኃይል አይተው «ጌታ ሆይ ስንጠፋ አይገድህምን)» ያሉ ለዚህ ነው፡፡ /ማር.4.35/፡፡ ከሁሉም በላይ ደግሞ ልንጠነቀቅ የሚገባው ሰይጣን እንዳያታልለን ነው፡፡ ምክንያቱም ቅዱስ ጳውሎስ እንደተናገረው የብርሃን መልአክ እስከሚመስል ድረስ ራሱን ይለውጣልና፡፡ /2ቆሮ.11.14/፡፡ እንዳለ፡፡ ምትሐታዊ የሆኑ ድንቅ ምልክቶችንም ያደርጋልና፡፡ /2ተሰ.2.3-9/፡፡ ሌላው ደግሞ ቤተ ክርስቲያናችን ውስጥ ካለው ነገር የምንጠራጠርበት ምንም ዓይነት ነገር መኖር የለበትም፡፡ ምክንያቱም ዛሬ በዓይነ ሥጋ ብቻ በመመልከት ጥቃቅን መስለው በሚታዩን ነገሮች መጠራጠር ከጀመርን ነገ ደግሞ የእግዚአብሔርን አዳኝነት እስከ መጠራጠር እንደርሳለንና ነው፡፡

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ኢይብቁል ብክሙ መሪር ሥርው

/መራራ ሥር አይብቀልባችሁ/ /ዕብ.12፡15/  
ዘገብርኤሏ

የአብርሃም ልጆች ነን የሚሉ ነገር ግን የአብርሃምን ሥራ የማይሠሩና የነቢዩ ዳዊት ልጆች ነን የሚሉ የእርሱን ፈለግ የማይከተሉ ዕብራውያንን ቅዱሱ ጳዉሎስ «መራራ ሥር አይብቀልባችሁ» ሲል መከራቸው፡፡ ዕብራውያን በእግዚአብሔር እናምናለን፤ የእሱ ልጆች ነን እያሉ ይመጻደቁ ስለነበሩ መልካም ሥራ በመሥራት ወደ እግዚአብሔር እንዳይቀርቡ የከለከላቸውን መራራውን ሥር እንዲያስወግዱ አሳሰባቸው፡፡ ሁሉን የሚያይና የሚያውቅ አምላከ ሰማይ ወምድር ኢየሱስ ክርስቶስ እነዚህን ውጫቸውን ያሳመሩ ነገር ግን ውስጣቸውን በኃጢአት ያሳደፉትንና በመራራ ሥር የተመሰለው ኃጢአት በውስጣቸው የበቀለባቸውን ጸሐፍትና ፈሪሳውያንን ሲገስጽ «እናንተ ግብዞች ጻፎች፤ ፈሪሳዉያን በውስጡ ቅድሚያና ስስት ሞልቶ ሳለ የጽዋውንና የወጭቱን ውጭ ስለምታጠሩ ወዮላችሁ፡፡» ብሏቸውል፡፡ /ማቴ.23፡25/

ኃጢአትን በሐልዮ ጸንሶ በነቢብ መውለድ፣ በነቢብ ወልዶም በገቢር ማሳደግ መራራ ሥር ነው፡፡ /ማቴ.24፡16/ ይህም ማለት ኃጢአትን ማሰብ አስቦም ሥራ ላይ ማዋል በአጠቃላይ በኃጢአት መውደቅ በሰው ልቡና ውስጥ የሚበቅል መራራ ሥር ነው፡፡ በዚህም «ሐሞትና እሬትም የሚያበቅል ሥር አይሁንባችሁ» /ዘዳ.18፡19/ የተባለውም የሰው ልጅ በመራራ ሥር፣ በሐሞትና በእሬት የተመሰለውን ኃጢአት ከሕይወቱ ካላራቀ መራራ ገሀነመ ዕሳት እጣ ፈንታው ይሆናል፡፡
ከላይ የጠቀስናቸው ሐሳቦች በሙሉ መራራ ሥር የተባለው ኃጢአት መሆኑን የሚያረጋግጡ ናቸው፡፡ ስለሆነም እስኪ በሕይወታችን ውስጥ ሊነቀሉ የሚገባቸው ከእግዚአብሔር መንግሥት የሚለዩንን መራራ ሥሮች በዝርዝር እንመልከት፡፡

1.ዝሙት

ዝሙት አእምሮን የሚያጐድል፣ ሰላምን የሚነሣ፣ ጤንነትን የሚያሳጣ፣ ሕይወትን የሚያበላሽ፣ ጸጋ እግዚአብሔርን የሚያሳጣ /የሚገፍፍ/ በሰው ልቦና ውስጥ የሚበቅልና መነቀል ያለበት መራራ ሥር ነው፡፡ ብዙ ታላላቅ አባቶች ክብራቸውን ያጡት በዝሙት እንደሆነ መጻሕፍት ያስረዳሉ፡፡ ለምሳሌ፡- እስራኤላዊያን ከሞአብ ልጆች ጋር በማመንዘራቸው ብኤልፌጐር የሚባል ጣዖት እንዲያመልኩ አደረጓቸው፡፡ ከዚህም የተነሣ እግዚአብሔርን በማስቆጣታቸው 24 ሺሕ ሕዝብ በአንድ ቀን ተቀስፏል፡፡ /ዘፍ.22፡37፣ ዘኁ.27፡1/ «ኃጢአትን የሚዘራ መከራን ያጭዳል» እንደተባለው፡፡ /ምሳ.22፡1ዐ/
ዝሙት፣ ሴሰኝነትና አመንዝራነት ቅድስናን ከሚያሳጡ ታላላቅ ኃጢአቶች ውስጥ የሚቆጠሩ ናቸው፡፡
የሰው ልጅ በእነዚህ ኃጢአቶች እንዳይወድቅ እግዚአብሔር አምላክ ሁሉን አዋቂ ነውና አንድ ለአንድ በመወሰን ጸንቶ እንዲኖር ጋብቻን ባርኮ ቀድሶ ሰጥቶታል፡፡ «መጋባት በሁሉ ዘንድ ክቡር፤ መኝታውም ንጹሕ ይሁን፣ ሴሰኞችንና አመንዝሮችን ግን እግዚአብሔር ይፈርድባቸዋል፡፡» እንዲል፡፡ /ዕብ.13፡4፣ 1ቆሮ.7፡1/ ዝሙት ከእግዚአብሔር መንግሥት የሚለይ መራራ ሥር ነው የተባለውም ለዚህ ነው፡፡ ሶምሶንም ጸጋውን እንዲገፈፍ ያደረገው ይህው በውስጡ የበቀለው መራራ ሥር ነው፡፡ /መሳ.17፡1/ ይህ ታላቅ ሰው ለእግዚአብሔር የተለየ ናዝራዊ ቢሆንም አንድ ናዝራዊ ማድረግ የሌለበትን የዝሙትን ተግባር ፈጽሞ በመገኘቱ ከክብሩ ተዋርዷል ኀይሉ ተነፍጎታል፡፡ /ዘኁ.6፡1/ ዛሬም ትእዛዛተ እግዚአብሔርን በመጣስና ዝሙት በመሥራት ከክብር እየተዋረድን ያለን ሰዎች ራሳችንን ልንመረምርና መራራውን ሥር በንስሐ በጣጥሰን በመጣል ወደ እግዚአብሔር ልንቀርብ ይገባል፡፡ ለሶምሶን እግዚአብሔር አምላክ ታላላቅ ውለታዎችን ቢውልለትም፤ እሱን ያስጨነቀው አምላክ ያደረገለት ውለታ ሳይሆን ከደሊላ በዝሙት የመውደቅ መንፈስ አእምሮውን አሳጥቶት ነበር፡፡ /መሳ.16፡17/ ይህች ሴት ቃሏን አጣፍጣ የዚህን የተመረጠ ሰው ሕይወት እንዳጠመደችው ዛሬም የብዙዎቹን ሕይወት በዝሙት የሚያጠምዱ እርኩስ መንፈስ ያደረባቸው መራራ ሥር የበቀለባቸው እንዳሉ ማስተዋል ይገባል፡፡
ከክብራችን እንዳንዋረድ የቅዱሳን አባቶቻችንን ፈለግ በመከተል ሥጋችንን ለነፍሳችን አስገዝተን መኖር ያስፈልጋል፡፡ ዓይኖቻችን ወደ ቅዱስ ሥጋውና ወደ ቅዱስ ደሙ የሚመለከቱ መሆን አለባቸው፡፡ «ልጄ ሆይ ወደ ጋለሞታ ሴት ልብህ አይባዝን በጐዳናዋ አትሳት፡፡ ወግታ የጣለቻቸው ብዙ ናቸውና፡፡» /ምሳ.7፡24/ በዝሙት ተወግተው ከወደቁት ወገኖች እንዳንደመር በየትኛውም ቦታ ጥንቃቄ ልናደርግ ያስፈልጋል፡፡

2.ትዕቢት

 ሳጥናኤልን ያህል ታላቅ መልአክ ከክብሩ ያዋረደው ሌላው መራራ ሥር ትዕቢት ነው፡፡ ትዕቢት በመራራ ሥር የተመሰለውም ከኔ በላይ ማን አለ በማለት የማይገባውን ይገባኛል እያሰኘ ሌላውን የመናቅ፤ ራስን ከፍ ከፍ የማድረግ መራራ መንፈስ ስለሚያበቅል ነው፡፡ «አንተ የንጋት ልጅ አጥቢያ ኮከብ ሆይ አንተ ወደ ሰማይ ዐርጋለሁ፣ ዙፋኔንም ከሰማይ ከዋክብት በላይ ከፍ ከፍ አደርጋለሁ አልህ፡፡ ነገር ግን ወደ ሲኦል ወደ ጉድጓድም ጥልቅ ትወርዳለህ፡፡» /ኢሳ.14፡12-16/ ብሎ የተናገረለት ሳጥናኤል በትዕቢቱ ምክንያት ነው፡፡ «ትዕቢተኛ የሆነውና ልቡ የሚሳሳው ከእኔ ጋር አይተባበርም፡፡» /መዝ.3፡5/ ተብለ የተነገረውን የእግዚአብሔርን ቃል ልናስብ ይገባል፡፡
ይሁን እንጂ ትናንት በቅድስት ቤተ ክርስቲያን እቅፍ ቅዱስ ሥጋውንና ቅዱስ ደሙን እየበላና እየጠጣ አድጎ በትዕቢት ምክንያት የበላበትን ወጭት ሰባሪ የሆነ ብዙ ነው፡፡ ክርስቲያን ነኝ እያለ በሀብቱ በጉልበቱ በእውቀቱ፣ በወገኑ የሚኩራራና የሚታበይም አለ፡፡ ይሁን እንጂ ሀብታሙ በደሃው ላይ፣ የተማረው ባልተማረውላይ አሠሪ በሠራተኛው ላይ የሚታበይ ከሆነ ክርስቲያን ነው ሊባል ከቶ አይችልም፡፡ እውነተኛ የእግዚአብሔር ልጆች መገለጫ፤ ያለው የሌለውን መርዳት፣ የተማረውም ላልተማረው ደሃ ተበደለ ፍርድ ተጓደለ ማለት፣ ስለ ፍቅረ እግዚአብሔር ሲባል ራስን ዝቅ ማድረግ ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያን የማገልገል ጸጋ ቢሰጠንም በቸርነቱ መሆኑን ማወቅ ይኖርብናል እንጂ ልንታበይ አይገባም፡፡ በሰንበት ትምህርት ቤት፣ በሰበካ ጉባኤ፣ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የምናገለግል ሁሉ የምናቀርበው የአገልግሎት መስዋዕት በእግዚአብሔር ቸርነት መሆኑን ልንገነዘብ ይገባል፡፡ ልክ «… የታዘዛችሁትን ሁሉ ባደረጋችሁ ጊዜ የማንጠቅም ባሪያዎች ነን ልናደርገው የሚገባንን አድርገናል በሉ፡፡» እንደተባለ፡፡ /ሉቃ.17፡1ዐ/
ስለዚህ ፈሪሃ እግዚአብሔር ሊኖረን እንጂ ልንታበይ አይገባም፡፡ «እግዚአብሔርን መፍራት ባለጠግነት ክብር ሕይወትም ነው፡፡» /ምሳ.22፡4/ እንዳለ ጠቢቡ በምሳሌው፡፡

 3. ማስመሰል

መመሳሰልና መስሎ መታየት፣ ለመመሳሰል መጣር የብዙዎች ችግር ነው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አንዳች ፍሬ ባገኝባት ብሎ ወደ አንዲት ዛፍ ሲጠጋ ፍሬ ያፈራች መስላ እንጂ አፍርታ ባለመገኘቷ ምክንያት ለዘላለሙ ፍሬ አይገኝብሽ ብሎ ረገማት፤ ወዲያውም ደረቀች፡፡ /ማቴ.21፡18/
ከዚህ ኀይለ ቃልም የምንረዳው በመስሎ መኖርና ሆኖ አለመገኘት የሚያመጣውን ርግማን ነው፡፡ ማስመሰል መራራ ሥር ነውና ሊነቀል ይገባዋል፡፡ ዛሬም ብዙ ሰው በአፉ የሃይማኖት ሰው ይመስላል፣ እውነታው ግን እንዲህ አይደለም፡፡ ብዙዎች ቤተ ክርስቲያን የሚሔዱ ጾም የሚጾሙ፣ ነገር ግን ከኃጢያት ያልተለዩ፣ በንስሐ መመለስን ችላ የሚሉ፣ ታቦት ሲነግሥ እልል ስለተባለ ብቻ እልል የሚሉ ከዚያ ሲወጡ ግን ኃጢአት ለመሥራት የሚጣደፉና በልባቸው የሸፈቱ ሰዎች የማስመሰሉን መራራ ሥር ከውስጣቸው በንስሐ ነቅለው መጣል አለባቸው፡፡ ሆኖ መገኘት እንጂ መስሎ መታየት አያድንምና፡፡ «ይህ ሕዝብ በከንፈሩ ያከብረኛል፣ ልቡ ግን ከኔ በጣም የራቀ ነው፡፡ የሰውም ሥርዓት የሆነ ትምህርት እያስተማሩ በከንቱ ያመልኩኛል፡፡» /ኢሳ.29፡13፣ ማቴ.5፡8/ እንደተባለው ዛሬም የብዙ ሰው አምልኮ የዚህ ትንቢት መፈጸሚያ ይመስላል፡፡ ስለዚህ ጥዋት ቤተ ክርስቲያን፤ ከሰዓት ቤተ ጣኦት በመሔድ ጊዜን በከንቱ ከማሳለፍ መቆጠብ ያሻል፡፡ ክርስቲያን ነኝ እያለ ጨሌውን፣ የዐውደ ነገሥቱን ጥንቆላ ማመን፣ መናፍስትን መጥራትና የመሳሰሉትን እየፈጸሙ መገኘት በልብ መሸፈት ነውና ልንመለስ ይገባል፡፡ «በሰማያት ያለው የአባቴን ፈቃድ የሚያደርግ እንጂ ጌታ ሆይ፤ ጌታ ሆይ፤ የሚሉኝ መንግሥተ ሰማያት የሚገቡ አይደሉም፡፡» /ማቴ.7፡21/ ተብሏልና፡፡
 መስለው ለመኖር የሞከሩ ብዙ ሰዎች ሲጎዱ እንጂ ሲጠቀሙ አላይንም፡፡ ግያዝ ከኤልሳዕ ጋር መስሎ ሲኖር ልቡ ግን ወደ ገንዘብ ሸፍቶ ስለነበር በለምጽ ተመታ፡፡ /2ኛ ነገ.5፡2ዐ/ የይሁዳንም ታሪክ ስንመለከት ከሐዋርያት ጋር ተመሳስሎ እየኖረ ልቡናው በፍቅረ ንዋይ ተነድፎ እንደነበር ነው፡፡ እናም እነዚህንና የመሳሰሉትን የፍቅረ ንዋይ፣ የስስት፣ የእምነት ጎደሎነት ወዘተ መራራ ሥሮች በቶሎ በንስሐ መነቃቀል ያስፈልጋል፡፡
 ካህኑም፣ ዲያቆኑም፣ ሰባኪውም፣ ዘማሪውም በአጠቃላይ የቤተ ክርስቲያን አገልጋይ ነኝ የሚል ሁሉም አገልግሎቱ ዋጋ የሚያገኘው ከእግዚአብሔር መሆኑን ከልብ በማጤንና ራሱን በመመርመር የጐደለውን ሊያስተካክል ይገባል፡፡ እያንዳንዷ ሥራችን የምትበጠርበት ጊዜ ይመጣልና፡፡ «መጻሕፍትም ተከፈቱ፤ ሌላ መጽሐፍም ተከፈተ፣ እርሱም የሕይወት መጽሐፍ ነው፡፡ ሙታንም በመጻሕፍት ተጽፎ እንደነበረ እንደሥራቸው መጠን ተከፈሉ፡፡ … እያንዳንዱ እንደሥራው መጠን ተከፈለ፡፡» እንዲል፡፡ /ራእ.2ዐ፡12/
 ስለዚህ መልካም ዋጋ ለማግኘት መልካም ሥራ ለመሥራት መጣር ይገባል፡፡ «አምላካችሁ እግዚአብሔርን ተከተሉ እርሱንም ፍሩ ትእዛዙንም ጠብቁ ቃሉንም ስሙ እርሱንም አምልኩ ከእርሱም ጋር ተጣበቁ» /ዘዳ.13፡4/ ስለተባልን ለመልካም ሥራ እሺ እንድንል ያስፈልጋል፡፡ «እሺ ብትሉ፣ ለእኔም ብትታዘዙ፣ የምድርን በረከት ትበላላችሁ፤ እምቢ ብትሉ ግን ብታምጹ ሰይፍ ይበላችኋል፤ የእግዚአብሔር አፍ ይህንን ተናግሯል» ተብሏልና፡፡ /ኢሳ.1፡19/

4. ዓላማ ቢስነት

ዓላማ የሌለው ሰው ከየት ተነሥቶ ወዴት መሔድ እንዳለበት የማያውቅ፣ ካሰበበት የማይደርስ ነው፡፡ ማንም ወደነዳው የሚነዳ፣ በጭፍን የሚጓዝ ሰው ዓላማ ቢስ ሊባል ይችላል፡፡ ዓላማ የሌለው ሰው በጀመረውና በተሠማራበት ተግባር ላይ ጸንቶ አይቆይም፡፡ በተለይ ክርስቲያን ዓላማ ከሌለው በትንሽ ነገር የሚፈተን፣ ሥጋዊ ፍላጐቱ ካልተሟላለት የማያገለግል፣ የሚያማርር፣ በሆነ ባልሆነው የሚያኰርፍ፣ መንፈሳዊነትን ያዝ፣ ለቀቅ የሚያደርግ የጸሎቱ፣ የጾሙ ዋጋ ዛሬውኑ እንዲከፈለው የሚፈልግ ይሆናል፡፡ የሚያገለግልበትንም ዓላማ ያልተገነዘበ ሰው በየደቂቃው እንዲመሰገን ይፈልጋል፡፡ ሰዎች ዓላማቸውን እንዲስቱ በልባቸው ውስጥ የማዘናጋትን ተግባር የሚፈጽም ጥንተ ጠላታችን ዲያብሎስ ስለሆነ ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ ይገባል፡፡ ቅዱሳን አባቶች በተለያዩ ፈተናዎች ውስጥ ቢያልፉም ዓላማን የመሳት መራራ ሥር በውስጣቸው አልበቀለም፡፡ በሁሉም ጸንተው በመቆማቸው ለክብር አክሊል በቅተዋል፡፡
 ሙሴ እስራኤልን በምድረ በዳ ይመራ በነበረበት ወቅት የተለያዩ ፈተናዎች ቢያጋጥሙትም ከዓላማው አልተዘናጋም፡፡ ይልቁንም ያህዌህ ንሲ /እግዚአብሔር ዓላማዬ ነው አለ እንጂ፡፡ /ዘዳ. 12፡15/
 ዮሴፍ ጽኑ ዓላማ ስለነበረው የተዘጋጀለትን የዝሙት ግብዣ እምቢ አለ፡፡ /ዘፍ. 39/
 ሶስና ልትሸከመው የማትችል የሚመስል ፈተና ቢያጋጥማት ንጽሕናዋን ክብሯን ጠብቃ፣ ለአምላኳ ታምና መኖርን ዓላማዋ ስላደረገች የመጣባትን ፈተና በጽናት፣ በታማኝነት፣ በንጽሕና በቅድስና ልታልፍ ችላለች፡፡ /መጽሐፈ ሶስና/
 ኢዮብ ዓላማው እግዚአብሔር ስለነበር ይፈራረቅበት የነበረውን መከራ፣ ሥቃይና ችግር ሊያልፍ ችሏል፡፡ ወርቅ በእሳት እንደሚፈተን ሁሉ ተፈትኖ፣ ነጥሮ ታላቅነቱን አስመስክሯል፡፡ /ኢዮ.2፡10/ በአንጻሩ ደግሞ ዓላማቸውን የሚያስት መራራ ሥር በውስጣቸው በመብቀሉ ምክንያት የተጐዱ ከክብራቸው ያነሡ ጥቂቶች አይደሉም፡፡
 ለምሳሌ ሳኦልን ብንመለከት እግዚአብሔር አምላክ ከሕዝበ እስራኤል ላይ ንጉሥ እንዲሆን ቢሾመውም የቅንዓት መንፈስ በውስጡ ስለበቀለ እግዚአብሔርን የሚያሳዝን ተግባር ሲሠራ እናያለን፡፡ /1ኛሳሙ. 11፡9፣15፡35/
ዛሬም ትናንት የቤተ ክርስቲያን ልጆች የነበርን፣ እግዚአብሔር ከፍ ስላደረገን፣ ስለሾመን ዓላማችንን የዘነጋን አንታጣምና ራሳችንን ልንመረምር ይገባል፡፡ ከዓላማችን እንድንስት የሚያዘናጉ ነገሮች በርካቶች ናቸው፡፡ ሰው ለገንዘብ፣ ለሥልጣን፣ ለሓላፊ ጠፊ ሀብት ብሎ ዓላማውን ይስታል፡፡ ይሁዳ ምንም እንኳን ከሐዋርያት አንዱ ሆኖ ቢቆጠርም ዓላማው መንግሥተ ሰማያትን መውረስ ሳይሆን ገንዘብን ማሳደድ ስለነበረ አምላኩን እስከ መሸጥ ደረሰ፡፡ «እንጀራዬን የበላ በእኔ ላይ ተረከዙን አነሣ፡፡» ተብሎ የተነገረው ትንቢት ተፈጸመበት፡፡ /መዝ.4ዐ፡9/ ይሄው ዛሬ የነፍሰ ገዳዮችና የክፉዎች ተምሳሌት ሆኖ ይነገራል፡፡ ስለዚህ «ከመልካም ሽቱ መልካም ስም ይሻላል፡፡» እንደተባለ ስማችን በክፉ እንዳይጠራ በዓላማችን እንጽና፡፡ /መክ. 7፡1/ ዓላማችን መንግሥቱን ለመውረስ፣ ስሙን ለመቀደስ ይሁን፡፡ እንደ ዴማስ ወደ ዓለም የሚመለስ መራራ ሐሳብ በውስጣችን እንዳይበቅል ጥንቃቄ እናድርግ፡፡ /2ኛጢሞ. 4፡9/

5. የጥርጥር መንፈስ

«የሚጠራጠር ሰው በነፋስ የተገፋና የተነቃነቀ የባህርን ማዕበል ይመስላል፡፡ ሁለት ሐሳብ ላለው፣ በመንገድም ሁሉ ለሚወላውል ለዚያ ሰው ከጌታ ዘንድ አንዳች የሚያገኝ አይምስለው፡፡» /ያዕ. 1፡6/ በማለት እንደተነገረው ተጠራጣሪ ሰው ከጌታ አንዳች ነገር አያገኝም፡፡
 በአሁኑ ወቅት ከጽናታችን እንድንናወጥ የሚያደርጉ ብዙ ነገሮች እንዳሉ ይታወቃል፡፡ ነገር ግን የተጠራበትን ዓላማ ጠንቅቆ የማያውቅ ክርስቲያን በጥርጥር ነፋስ ተነቅሎ ይገነደሳል፡፡ ስለዚህ ጊዜው ከፍተኛ ጥንቃቄ የሚሻው በመሆኑ በማስተዋል መራመድ ያስፈልጋል፡፡
 ቅዱሳን ሐዋርያት በመንፈስ ቅዱስ ገላጭነት ይመጣ ዘንድ ስላለው ክህደትና ሐሳዊ መሲህ «… የሚፈጥንን ጥፋት በራሳቸው ላይ እየተሳቡ የሚያጠፉ ኑፋቄን አሾልከው ያገባሉ፤ … በእነርሱም ጠንቅ የእውነት መንገድ ይሰደባል፡፡» /2ጴጥ.2፡1/ በማለት ተናግረዋል፡፡ በመሆኑም የክርስቶስን አምላክነት የሚጠራጠርና የሚያጠራጥር፣ በቅዱሳን ላይ አፉን የሚከፍት ሐሳዊ መሲህ ቢነሣ የሚያስደንቅ መሆን የለበትም፡፡ ለምን ቢሉ ትንቢቱ ይፈጸም ዘንድ ግድ ነውና፡፡ ዮሐንስም ስለዚህ ነገር «አውሬው ታላቅ ነገርና ስድብን የሚናገርበት አፍ ተሰጠው … እግዚአብሔርንም ለመሳደብ ስሙንና ማደሪያውንም፣ በሰማይም የሚያድሩትን ሊሳደብ አፉን ከፈተ፡፡» ብሎ ጽፏል፡፡ /ራእ.13/
ስለዚህ በልባችን የሚበቅለውን የጥርጥር መንፈስ ከውስጣችን ነቅለን ልንጥል ያስፈልጋል፡፡ «ከራሳችሁ ጽናት እንዳትወድቁ ተጠንቀቁ፡፡ /2ጴጥ.3፡17/ እንደተባልነው ጥንቃቄ ልናደርግ ያስፈልጋል፡፡
በአጠቃላይ መራራ ሥር ኃጢአትና ክርስቲያናዊ ምግባር በአንድ ሰውነት ላይ ሊበቅሉ የማይገባቸው እንክርዳድና ፍሬ ናቸው፡፡ በመሆኑም በንስሐ መከር መለየት ይኖርብናል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም የመራራ ሥራ ፍሬዎችን የሥጋ ሥራ በማለት ገልጿቸዋል፡፡ «አስቀድሜ እንዳልኩ እንደዚህ ያሉትን የሚያደርጉ የእግዚአብሔርን መንግሥት አይወርሱም ብሏል፡፡ ገላ. 5፡21» ስለዚህ ክርስቲያናዊ ሕይወት እንዲያብብ የክፋት ሥራ የሆኑ ኃጢአቶችን በንስሐ እና በተጋድሎ በተለይም ዝሙት፣ ትዕቢት፣ ማስመሰል፣ ዓላማ ቢስነትና የጥርጥር መንፈስ የመሰሉ መራራ ስሮች በጥንቃቄ መንቀልና ማራቅ ያስፈልገናል፡፡ መራራ ሥሮችን ነቅለን የመንፈስ ፍሬያትን በሰውነታችን እናበቅል ዘንድ የእግዚአብሔር ቸርነት የቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት አይለየን፡፡

                                                    

                                                             ወስብሐት ለእግዚአብሔር

የመጥምቀ መለኮተ ቅዱስ ዮሐንስ ሕይወትና አገልግሎት ክፍል ሁለት

                                 ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ እና ነቢዩ ኤልያስ

 ቅዱስ ዮሐንስ በበርካታ መንገዶች ከነቢዩ ኤልያስ ጋር ተያይዟል፡፡ነቢዩ ሚልክያስ ስለ ቅዱስ ዮሐንስ መምጣትና መንገድ ጠራጊነት ሲናገር እንዲህ ብሎ ነበር፡፡

የመጥምቀ መለኮተ ቅዱስ ዮሐንስ ሕይወትና አገልግሎት ክፍል አንድ

በቤተ ክርስቲያናችን ከመስከረም 1 እስከ 7 ያለው ጊዜ  ዘመነ ዮሐንስ ይባላል፤ ሳምንቱ የቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ሕይወቱ፣ትምህርቱና ምስክርነቱ የሚታሰቡበት ነው ፡፡

test page

ስብከት

ቅድስት ቤተክርስቲያን አምልኮቷን የምትፈጽምበት እጅግ የተደራጀ ሥርዐተ አምልኮ አላት፡፡ ከዚህ ሥርዓተ አምልኮ አንዱ ክፍል ዓመታዊ የምስጋና መርሐ ግብር እና የሥርዓተ ትምህርት ነው፡፡ ይህም በሁለት መልኩ የተደራጀ ነው፡፡

ሀ. ቀናትን መሠረት በማድረግ

በእግዚአብሔርና በሰው ልጆች ግንኙነት ውስጥ ጥልቅ ቦታ የሚሰጣቸው ድርጊቶች እና ክንውኖች በዓመቱ ውስጥ ቀናት ተመድበውላቸው በበዓላትና በአጽዋማት መልክ ይታሰባሉ፡፡ ቅድስት ቤተክርስቲያን እነዚህን በዓላትና አጽዋማት የምታከብርበት ዓመታዊ መርሐ ግብር እና በበዓላቱና በአጽዋማቱ የሚታሰበውን ነገር አስመልክቶ አባላቶችን የምታስተምርበት ሥርዓተ ትምህርት አላት፡፡

እንደዚህ ባለ መርሐ ግብር ከሚታሰቡት መካከል ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዘመነ ሥጋዌው ያደረጋቸው ነገሮችና ያስተማራቸው ትምህርቶች /ፅንሰት፣ ልደት፣ ጥምቀት፣ ስቅለት፣ ትንሳኤ፣ ዕርገት፣ ደብረ ታቦር፣ምጽአት/፤ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም በዓላት  /ልደቷ፣ ዕረፍቷ፣ ቤተመቅደስ መግባቷ፣ ድንቅ ተአምራት ያደረገችባቸው ዕለታት/፤፣ የቅዱሳን በዓላት /ልደታቸው፣ ዕረፍታቸው፣ ተአምራት ያደረጉባቸው. . / ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡

ለ. እሁዶችን /ሳምንታትን/ መሠረት በማድረግ

በዓመቱ ውስጥ ያሉት ቀናት/ከመስከረም 1 እስከ ጳጉሜን 5/ ብቻ ሳይሆኑ እሁዶቹም /ሳምንታቱም/ የተለያዩ ነገሮች ይታሰቡባቸዋል፡፡ በዓመቱ ውስጥ ባሉት እሁዶች /ሳምንታት/ በእያንዳንዳቸው የሚቀርበው ምስጋና እና የሚሰጠው ትምህርት ምን እንደሆነ የሚገልጽ መርሐ ግብር እና ሥርዓተ ትምህርት አላት፡፡ ለምሳሌ ከመስከረም 1 እስከ 7 ድረስ ያለው እሁድ /ወይም በዚህ እሁድ የሚጀምረው ሳምንት/ «ዮሐንስ አኅድአ»፣«ዮሐንስ መሰከረ ይባላል፡፡ የቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ሕይወት እና ምስክርነት የሚታሰብበት ነው፡፡

መስከረም 8 ቀን እሁድ ቀን ቢውል ያ እሁድ «ዘካርያስ» ተብሎ ይጠራና የመጥመቁ ዮሐንስ አባት የካህኑ የዘካርያስ ነገር ይታሰብበታል፡፡

ከመስከረም 9 እስከ 17 ያለው እሁድ /እና በዚህ እሁድ የሚጀምረው ሳምንት/ «ፍሬ» ይባላል፡፡ በዚህ እሁድ እግዚአብሔር ለምድር ፍሬን እንደሚሰጥ ይታሰባል፡፡
በዚህ መልኩ በዓመቱ ውስጥ ባሉት እሑዶች በሙሉ ምን እንደሚታሰብ የሚገልጽ መርሐ ግብርና ሥርዓተ ትምህርት አለ፡፡ ይህም በተለያዩ ወቅቶች ያለውን የአየር ጠባይ እና የግብርና እንቅስቃሴ ያገናዘበ ነው፡፡

 

በእነዚህ ዕለታት ምስጋና የሚቀርብበት እና ትምህርት የሚሰጥበትን ጉዳይ /ርእስ/ መወሰን ብቻ ሳይሆን በጉዳዩ ላይ ዝርዝር ነገሮችም ተዘጋጅተዋል፡፡

«ስንክሳር» የሚባለው መጽሐፍ ከመስከረም አንድ እስከ ጳጉሜን 5/6 ድረስ የሚታሰቡ ቅዱሳንን እና ክንውኖችን ዝርዝር ታሪክ ይዟል፡፡

«ግጻዌ» የሚባለው መጽሐፍ በየዕለቱ /በየእሁዱ/ ከሚታሰበው ጉዳይ ጋር ተያያዥነት ያላቸው አምስት የመጽሐፍ ቅዱስ ምንባባት /ከመልእከታተ ጳዉሎስ፣ ከሰባቱ መልእክታተ ሐዋርያት፣ ከሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ፣ ከመዝሙረ ዳዊት፣ ከወንጌል/ መርጦ ያቀርባል፡፡

የቅዱስ ያሬድ የዜማ መጻሕፍትም /ድጓ፣ ዝማሬ፣ምዕሪፍ፣ ዝማሬ መዋስዕት/ በዚህ መርሐ ግብር መሠረት የተዘጋጁ ሲሆኑ በየዕለቱ ስለሚታሰቡት ነገር ዝርዝር እና ጥልቅ የሆኑ ትምህርቶችን እና ምስጋናዎችን የያዙ ናቸው፡፡

በዚህ «ስብከት» በሚለው ዓምድ ሥር ይህንን መርሐ ግብር፣ ሥርዓተ ትምህርት መሠረት አድርገን ትምህርቶችን እናቀርባለን፡፡ በአጠቃላይ በዚህ ዓምድ ስር የሚቀርቡት ትምህርቶች ሦስት ዓይነት ናቸው፡፡
1. ሳምንታዊ ስብከት– በዚህ ንዑስ ዓምድ ስር በእያንዳንዱ እሁድ/ሳምንት/ የሚታሰቡትን ጉዳዮች አስመልክቶ ትምህርቶች ይቀርባሉ፡፡
2. ወቅታዊ ስብከት– በዚህ ንዑስ ዓምድ ስር ቀናትን መሠረት አድርገው ከሚከበሩት በዓላት መካከል ዋና ዋናዎቹን በተመለከተ ትምህርቶች ይቀርባሉ፡፡
3. ሌሎች– ይህ ንዑስ ዓምድ በተለያዩ ርእሰ ጉዳዮች ላይ የተዘጋጁ ስብከቶች የሚቀርቡበት ነው፡፡

አዘጋጆቹን በጸሎት በማሰብ፣ በሚቀርቡ ስብከቶች ላይ አስተያየት በመስጠትና ስብከቶችን በመላክ ለዚህ ዓምድ መጠናከር ሁላችንም የበኩላችንን አስተዋጽኦ እናድርግ፡፡ እግዚአብሔር ሐሳባችንን እንድንፈጽም ቅዱስ ፈቃዱ ይሁንልን፡፡

ርእሰ ዓውደ ዓመት ቅዱስ ዮሐንስ

በዳዊት ደስታ

እንኳን ለአዲሱ ዓመት በሰላምና በጤና አደረሳችሁ፡፡ ዘመነ ማቴዎስም፣ ዘመነ ማርቆስም፣ ዘመነ ሉቃስም ሆነ ዘመነ ዮሐንስ በአራቱም ዘመናት አስቀድሞ ርእሰ ዓውደ ዓመት ቅዱስ ዮሐንስ ይዘከራል፡፡ ዮሐንስ የስሙ ትርጉም «ጸጋ እግዚአብሔር» ማለት ነው፡፡ ዘመናት ዘመናትን እየወለዱ፣ ሰዓታት ደቂቃን ቅጽበትን /ሰኮንድን/ ሳይቀር እየሰፈሩ/እየቆጠሩ/ ዕለታት ሳምንታትን፣ ሳምንታት ወራትን፣ ወራት ዓመታትን አሁን ላለንበት ዘመን ደርሰናል፡፡ ዓውደ ዓመት በግእዝ ሲሆን በአማርኛ የዘመን መለወጫ/ ቅዱስ ዮሐንስ፣ ዕንቁጣጣሽ እየተባለም ይጠራል፡፡

ቅዱስ ማርቆስ ወንጌሉን ሲጽፍ «የእግዚአብሔር ልጅ የኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌል መጀመሪያ እነሆ መንገድህን የሚጠርግ መልእከተኛዬን በፊትህ እልካለሁ የጌታን መንገድ አዘጋጅ ጥርጊያውንም አቅኑ እያለ በምድረ በዳ የሚጮኽ ሰው ድምፅ» ተብሎ በኢሳይያስ እንደ ተነገረ የነቢዩ ዘካርያስ ልጅ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ በዘመነ ብሉይ መጨረሻና በዘመነ ሐዲስ መጀመሪያ ላይ ተነሥቶ «መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ» እያለ ስለ ክርስቶስ አዳኝነት እየመሰከረ በምድረ በዳ የንስሐን ጥምቀት እያጠመቀ ለኃጢአት ሥርየት እየሰበከ መጣ ብሎ በዘመነ ወንጌል የመጀመሪያ ምዕራፍ ገልጾታል፡፡ /ማር.1.40፤ኢሳ.40.3-4/፡፡

የመጥምቁ ዮሐንስ ተግባር ለዘመነ ወንጌል በር ወይም መነሻ ሆኖ መገኘቱን በመረዳት የቤተክርስቲያን አበው የበዓላቱን ድንጋጌ በወሰኑበት ጊዜ የመጥምቁ ዮሐንስ መታሰቢያ በዓል የኢትዮጵያ ርዕሰ ዓውደ ዓመት በሚሆን መስከረም አንድ ቀን እንዲከበር በየዓመቱ የዘመኑ መጀመሪያ በእርሱ ስም እንዲጠራ አባቶች ደንግገዋል፡፡ / ድርሳነ ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ገጽ 1ጠ 3/ ይህንንም በዓል አባቶቻችን በርእሰ ዓውደ ዓመት ማክበር እንደሚገባ አስበው ያደረጉት ነው፡፡ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ በሰማዕትነት ያረፈበት ቀን ሆኖ አይደለም፡፡ ለአዲሱ ዓመት መጀመሪያ ወይም ርእሰ ዓውደ ዓመት «ቅዱስ ዮሐንስ» ይባላል፡፡ መጽሐፈ ስንክሳር የዓመቱን መጀመሪያ /መስከረምን/ ሲያትት «ይህ የመስከረም ወር የተባረከ ነው እርሱም የግብጽና የኢትዮጵያ ዓመቶች መጀመሪያ ነው በማለት ያስረዳል፡፡ የዚህ ወር ቀኑና ሌሊቱ እኩል 12 ሰዓት ነው፡፡ ከዚህ በኋላ ከመስከረም አንድ ቀን ጀምሮ ቀኑ እየጎደለ ይሔዳል፡፡

ከዚህ በመቀጠል በዓሉ በተለያየ ስያሜ ስለመጠራቱና ትርጓሜያቸውን እንመለከታለን፡፡

ዘመን መለወጫ

አስቀድመን ስለ ቅዱስ ዮሐንስ ማንነትና የዘመን መለወጫ መግቢያው ላይ በስሙ ስለመጠራቱ ተመልክተናል፡፡ ዘመን መለወጫ ደግሞ ለምን እንደተባለና ለምን መስከረም ወር ላይ እንደሆነ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን እንዲህ በማለት ያትታሉ፡፡ ሲያትቱም ብርሃናት/ፀሐይ፣ ጨረቃ፣ ከዋክብት/ የዓመት ዑደታቸውን በጳጉሜ ወር ጨርሰው በመስከረም ወር ስለሚጀምሩ ነው፡፡ ያን ጊዜ ሌሊቱም ከቀኑ ጋር ይተካከላል፡፡ ዓመቱንም ጠንቀቀው ቢቆጥሩት 364 ቀናት ይሆናል፡፡ ለዘመን መታወቂያ ይሆን ዘንድ ፀሐይና ጨረቃ ከዋክብትን ፈጠረ ይላልና /ሔኖክ.21.49/፡፡ በሌላ በኩልም በዘመነ ኖኅ ዓለምን ውኃ አጥለቅልቋት ከቆየ በኋላ ዳግመኛ ከነበረው ውኃ የተገለጠችበት ወር «በመጀመሪያም ወር በምድር ታየች የንፍር ውኃው ከምድር ደረቀ» የሚለውን መሠረት አድረገው የአቡሻኽር ሊቃውንት የዘመን መለወጫን ታሪካዊ አመጣጥ ያስረዳሉ፡፡/ኩፋ.7.1/
በመሠረቱ ዘመን ተለወጠ ሲባል የሚለወጡት ወራቱ ብቻ አይደሉም፡፡ በወቅቱ የሚከሰቱት/የተከሰቱት/ መልካምም ሆነ ክፉ ነገር /ገጠመኝ/ ሲሆን ወራቶቹ ግን ያው በየዓመቱ እየተፈራረቁ ይመጣሉ፡፡ ዘመን መለወጫ ላይ የሰው ልጆች ሕይወት ሊለወጥ ይገባል፡፡ ተማሪው ተምሮ ወደቀጣዩ ክፍል /ደረጃ/ የሚለወጥበት፣ ገበሬው የክረምቱን ወራት በሚገባ ተጠቅሞ የሚቀጥለውን የበጋ ወራት የሚቀበልበት፣ ሠራተኛው የክረምቱን ዝናብ ታግሶ የፀሐይን ወራት የሚቀበልበት ሌላውም እንደዚያ ሆነው ወራቶቹ በዚያ ዘመን ያለው የተፈጥሮ ክስተቶች የሚለወጥበት ዘመን ተለወጠ እየተባለ ይነገራል፡፡

እንቁጣጣሽ

ዓመታት ተፈጽመው አዲስ ዓመት ስንጀምር ቅዱስ ዮሐንስ፣ ዓውደ ዓመት፣ አዲስ ዓመት ፣ እንቁጣጣሽ እየተባለ ይጠራል፡፡ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን እንደሚያስረዱት እንቁጣጣሽ የሚለው ስያሜው አመጣጥ ወይመ ጥንተ ታሪክ በመጀመሪያ ኖኅ ለሦስቱ ልጆቹ አህጉራትን በዕጣ ሲያካፍላቸው አፍሪካ ለካም ደረሰችው፡፡ በአፍሪካ ምድርም ሲገባ በመጀመሪያ ያረፈው በኢትዮጵያ ነበር፡፡ ሀገሪቱም በአደይ አበባ አሸብርቃ ነበር፡፡ ወሩ ወርኃ መስከረም በመሆኑ ደስ ብሎት «ዕንቁ ዕጣ ወጣሽልኝ» ይህችን ወቅት እንቁጣጣሽ ብሏታል፡፡ ሁለተኛው የሀገራችን ንግሥት ንግሥተ ሳባ የንጉሥ ሰሎሞንን ዜና ጥበብ እየሰማች ስታደንቅ ትኖር ነበር፡፡ በጆሮዋ የሰማችውን በዓይኗ ዓይታ ለመረዳት ስለፈለገች በግመሎች ላይ ሽቱና እጅግ ብዙ ወርቅ እንዲሁም በኢትዮጵያ የሚገኝ በኢየሩሳሌም የማይገኝ ልዩ ልዩ ገጸ በረከት አስጭና ከብዙ ሠራዊት ጋር ወደ ኢየሩሳሌም ገባች፡፡ ከንጉሡ ሰሎሞንም ጋር ተገናኝታ የያዘችውን ገጸ በረከት ከሰጠችው በኋላ ብዙ ነገሮችን ጠየቀችው፡፡ እርሱም አንድ ነገር ላይ ሰውሮ ሁሉንም ገለጸላት፡፡ ቤተ መንግሥቱንም በቤተ መንግሥቱ የሚገኙ እጅግ በጣም የከበሩ ዕቃዎችን ሁሉ አስጎበኛት፡፡ ሲያበቃ «ዕንቁ ለጣትሽ ጌጥ ይሁንልሽ» ሲል እጅግ በጣም የከበረ ዕንቁ አበረከተላት/ሰጣት/፡፡ ወሩም ወረኃ መስከረም ነበር፡፡ ከዚህ በመነሣት እንቁጣጣሽ የሚለው መጥቷል፡፡ አሁን ከሚፈጸመው ሥነ ሥርዓት ደርሶ በመፈጸም ላይ ይገኛል፡፡ የሚከበረውም መስከረም አንድ ቀን ነው፡፡ አንድም «ዕንቁ ዕፅ አወጣሸ» ብሎ የአበባውን መፈንዳትን ያስረዳናል፡፡
በዚህ በአዲሱ ዓመት የሁለተኛው ሺሕ ማብቂያና የሦስተኛው ሺሕ መግቢያ ላይ እንገኛለን፡፡ የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ሁለት ሺሕ ዓመተ ምሕረት ያሳለፈቻቸውን መልካም ሥራዎችና የደረሰባትን መጥፎ ሥራዎችን አልፋ አሁን ላለው ትውልድ ደርሳለች፡፡ ይሕ ትውልድ ደግሞ በሦስተኛው ሺሕ ዓመት እምነቷን፣ ሥርዓቷን፣ ትውፊቷን አውቆ ለሚቀጥለው ትውልድ የማስተላለፍ አደራ አለበት፡፡
                           
ለዚህም የሚረዳውን ገዳማትና አድባራትን በማጠናከር ስብከተ ወንጌልን ለማስፋፋት ዘመናዊ አስተዳደር በመዘርጋት ከእኅት አብያተ ክርስቲያናት ጋር ጥሩ ግንኙነት በማድረግ የበኩሉን ሊወጣ ይገባዋል፡፡
ሺሕ ዓመቱ ሲለወጥ በዋዜማው ላይ በምንገኘኝበት ወቅት በእነዚህ ነገሮች ላይ ተቀራርቦ በመሥራት የሰው ዘር በሙሉ መንግሥተ ሰማያትን ለመውረስ ዝግጁ እንዲሆን ማድረግን ገንዘብ ልናደርግ ይገባል፡፡

                                             

                                                          ወስብሐት ለእግዚአብሔር