30

እረኝነት እንደ አፍርሃት ሶርያዊ አስተምህሮ

ታኅሣሥ 24/2004 ዓ.ም

ትርጉም

በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ

መግቢያ

አፍርሃት ያዕቆብ ዘንጽቢን እና “የፋርሱ ጠቢብ” በሚሉ ስያሜዎቹ የሚታወቅ አባት ሲሆን በዐራተኛው ክፍለ ዘመን መግቢያ ላይ የተነሣ ሶርያዊ ተጠቃሽ  ጸሐፊ ነው፡፡ በእርሱ ዘመን ማኅልየ ማኅልይ ዘሶርያና የቶማስ ሥራ የሚባሉት ሥራዎች እንደሚታወቁ ይታመናል፡፡ ስለአፍራሃት የሕይወት ታሪክ ብዙ የሚታወቅ ነገር ባይኖርም አንዳንድ ጥንታዊ ታሪክ ጸሐፊያን አፍራሃት በአሁኑዋ ኢራቅ ትገኝ በነበረችው ማር ማታያ ተብላ በምትታወቀው ገዳም ሊቀ ጳጳስ እንደነበረ ጽፈው ይገኛሉ፡፡ ይህ ግን ተቀባይነት የለው፡፡ አፍራሃት ሃያ ሦስት ድርሳናትን የጻፈ ሲሆን እነርሱም የተለያዩ ርእሶች ያሉዋቸው ናቸው፡፡ እርሱ ከጻፈባቸው ድርሰቶች መካከል ስለእምነት ፣ ስለፍቅር፣ ስለጾም ፣ ስለጸሎት፣ በዘመኑ ስለነበረው የቃልኪዳን ልጆችና ልጃገረዶች፣ ስለትሕትና ጽፎአል፡፡ አፍርሃት ከቅዱስ ኤፍሬም ጋር ለሶርያ ሥነ ጽሑፍ ፋና ወጊ የሆነ ጸሐፊ ነው፡፡  እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ በእረኝነት ላይ የፃፈውን እንመለከታለን፡፡

እረኞች የሕይወት ምግብን ይሰጡ ዘንድ በመንጋው ላይ የተሾሙ አለቆች ናቸው፡፡ መንጋውን የሚጠብቅና ስለእነርሱ የሚደክም እረኛ እርሱ መንጋውን ለሚያፈቅረውና ራሱን ስለመንጎቹ ለሰጠው መልካም እረኛ እውነተኛ ደቀመዝሙር ነው፡፡ ነገር ግን መንጋውን ከጥፋት የማይመልስ እርሱ ለመንጋው ግድ የሌለው ምንደኛ ነው፡፡

እናንተ እረኞች ሆይ በጥንት ጊዜ የነበሩትን ቅዱሳን እረኞችን ምሰሉአቸው፡፡ ያዕቆብ የላባን በጎች ያሰማራ፣ በትጋትና በድካም ይጠብቅ30 ነበር፡፡ በዚህም ከአምላኩ ዘንድ ዋጋ አግኝቶበታል፡፡ አንድ ወቅት ያዕቆብ ለላባ  “ሃያ ዓመት ሙሉ ከአንተ ጋር ነበርሁ በጎችህና ፍየሎችህ አልጨነገፉም የመንጎችህንም ጠቦቶች አልበላሁም አውሬ የሰበረውን አላመጣሁልህም ነበር፤ እኔ ስለ እርሱ እከፍልህ ነበርሁ፤ በቀንም በሌሊትም የተሰረቀውን ከእጄ ትሻው ነበር፡፡ የቀን ሀሩር የሌሊት ቁር ይበላኝ ነበር ፤ እንቅልፍ ከዐይኔ ጠፋ”(ዘፍ.፴፩፥፴፰-፴፱)ብሎት ነበር፡፡  እናንተ እረኞች ይህን እረኛ ለመንጎቹ ምን ያህል እንዲጠነቀቅ  አስተዋላችሁን? በሌሊት እንኳ እነርሱን ለመጠበቅ በትጋት ያለእንቅልፍ የሚተጋ እነርሱንም ለመመገብ በቀን  የሚደክም  እውነተኛ እረኛ ነበር፡፡

ዮሴፍና የእርሱ ወንድሞች ሁሉ እረኞች ነበሩ፤ ሙሴ የበጎች እረኛ ነበር፤ ዳዊትም እንዲሁ እረኛ ነበር፡፡ አሞጽም ላሞችን ያግድ ነበር፡፡ እነዚህ ሁሉ መንጎቻቸውን በመለመለመ መስክ ማሰማራት የሚያውቁ እረኞች ናቸው፡፡ ወዳጄ ሆይ  እግዚአብሔር እነዚህን እረኞች አስቀድመው በጎችን በኋላም ሰዎችን እንዲጠብቁ ስለምን እንዳደረጋቸው ተረዳህን? መልሱ ግልጽ ነው፤ መንጎቻቸውን እንዴት መጠበቅና ስለእነርሱ ሲሉ ምን ያህል መድከም እንዳለባቸው ሊያስተምራቸው በመፈልጉ ነበር፡፡ ይህንን የእረኝነት ሓላፊነት ከተማሩ በኋላ ለእረኝነት ተቀቡ፡፡ ያዕቆብ የላባን በጎች በብዙ ድካምና ትጋት ጠበቀ፤ በለመለመ መስክም አሰማራ፡፡ ከዛም ልጆቹን በአግባቡ ወደ መምራት ተመለሰ፣ የእረኝነት ሙያንም ለልጆቹ አስተማረ፡፡ ዮሴፍ በጎችን ከወንድሞቹ ጋር በመሆን  ይጠብቅ ነበር፡፡ ስለዚህም በግብጽ እጅግ ብዙ ሕዝብን ይመራና ልክ እንደ መልካም እረኛ ያሰማራ ዘንድ ተሾመ፡፡ ሙሴ የአማቱን በጎች ይጠብቅ ነበር፡፡

 

በመቀጠል ወገኖቹን ይመራ ዘንድ ተመረጠ፡፡ እርሱም እንደ መልካም እረኛ ሕዝቡን በለመለመ መስክ አሰማራ፡፡ ሕዝቡ የጥጃ ምስልን ሠርቶ እግዚአብሔር አምላክን በማሳዘናቸው ምክንያት ሊያጠፋቸው ቆርጦ ሳለ ሙሴ ስለሕዝቦቹ ተገብቶ እግዚአብሔር አምላክ ይቅር እንዲላቸው ዘንድ “አሁን ይህን ኃጢአታቸውን ይቅር በላቸው፤ ያለዚያ ግን ከጻፍከው መጽሐፍህ እባክህ እኔን ደምስሰኝ” (ዘጸአ.፴፪፥፴፪) ብሎ ጸለየ፣ እግዚአብሔር አምላኩን ተለማመነው፡፡ በመንጎቹ ፈንታ ነፍሱን የሚሰጥ እርሱ እጅግ መልካም እረኛ ነው፡፡ ስለሚመራው ሕዝብ ነፍሱን የሚሰጥ እርሱ ትክከለኛ መሪ ነው፡፡ እርሱ ስለመንጎቹ ደጀን ሆኖ የሚጠብቅና የሚመግብ ርኅሩኅ አባት ሊስኝ የሚገባው፡፡ መንጋውን እንዴት ማሰማራት እንደሚችል የሚያውቀው አስተዋዩ እረኛ ሙሴ እጁን ጭኖ መንፈሱን ላሳደረበት ለመንፈስ ልጁ ለኢያሱ ወለደ ነዌ፣ የእግዚአብሔርን መንጋ እንዲያሰማራ የእስራኤልንም ሠራዊት እንዲመራ የእረኝትን ሙያ አስተምሮት ነበር፡፡ እርሱ ጠላቶቹን ሁሉ ድል በመንሳትና ሀገራቸውንም በመውረስ፣ የመሰማሪያ መስክ በመስጠትና ምድሪቱንም ያርፉባትና ለበጎቻቸውም ማሰማሪያ ያገኙ ዘንድ አድርጎ አካፈላቸው፡፡

 

እንዲሁ ንጉሥ ዳዊት የአባቱን በጎች ይጠብቅ ነበር፡፡ ከዚህም ነው ሕዝቡን ይመራ ዘንድ የተቀባው፡፡ እርሱ ከልቡ ሕዝቡን ወደ አንድነት መራ፤ በእጁም ጥበብ መንጋውን አሰማራ፡፡ ዳዊት መንጎቹን ወደ መቁጠር በመጣ ጊዜ በእነርሱ ላይ የእግዚአብሔር ቁጣ ነደደ፤ ሕዝቡም እግዘአብሔር ባመጣው ቸነፈር ምክንያት ማለቅ ጀመረ፡፡ ዳዊት ግን በመንጎቹ ምትክ እርሱና ቤቱ ላይ ቅጣቱ እንዲፈጸም ጠየቀ፡፡ በጸሎቱ ስለእነርሱም “ጌታ ሆይ እኔ በድያለሁ፤ ጠማማም ሥራ አድርጌአለሁ፤ እነዚህ በጎች ግን እነርሱ ምን አደረጉ፤ እጅህ በእኔና በአባቴ ቤት ላይ አንድትሆን እለምንሃለሁ፡፡”(፪ሳሙ.፳፬፥፲፯)ብሎ እግዚአብሔር አምላክን አጥብቆ ተማጸነ፡፡ ነገር ግን ስለመንጎቻቸው ግድ ስለሌላቸው እረኞች፣ ለእነዚያ እራሳቸውን ብቻ ስለሚያሰማሩ እረኞች ነቢዩ እንዲህ ይወቅሳቸዋል “መንጎቼን የምታጠፉና የምትበትኑ እናንተ እረኞች ሆይ የጌታን ቃል ስሙ እግዚአብሔር እንዲህ ብሎአል፡፡ እረኛ መንጎቹን እንዲጎበኝ አንዲሁ እረኞችን የምጎበኝበት ጊዜ ይመጣልና ወዮላችሁ፡፡  በዚያን ጊዜ በጎቼን ከእጃችሁ እፈልጋቸዋለሁ፡፡

 

እናንተ ሰነፍ እረኞች ሆይ ከበጎቼ ፀጉር ለበሳችሁ፡፡ ከሰባውም ተመገባችሁ በጎቼን ግን አላሰማራችሁም፣ የታመመውን አላዳናችሁም፣ የተሰበረውን አልጠገናችሁም፣ የደከመውን አላበረታችሁም የጠፋውንና የባዘነውን አልፈለጋችሁም፣ ብርቱውንና የሰባውን አሰማራችሁ ነገር ግን እነርሱን በግፍ አጠፋችኋቸው፡፡ እናንተ የሰባውን ገፋችሁ በላችሁ፣ ከእግራችሁ ሥር ያለውን ረገጣችሁ፡፡ እናንተ ከጥሩ ውኃ ትጠጣላችሁ ከእናንተ የተረፈውን ውኃ ግን በእግራችሁ ታደፈርሳላችሁ፡፡ የእኔ በጎች እናንተ ባጠፋችሁት መስክ ታሰማሯቸዋላችሁ፡፡ በእግራችሁም ያደፈረሳችሁትንም ውኃ ታጠጧቸኋላችሁ” ይላል፡፡ (ዘካ. ፲፩፥፲፭-፲፯)  እነዚህ እረኞች ስስት የሠለጠነባቸው፣ የማያስተውሉ እረኞች እና ባለሙያተኞች ናቸው፡፡ እነዚህ መንጎቻቸውን አይመግቡም ወይም አይጠብቁም ወይም ለተኩሎች አሳልፈው የሚሰጡ ጨካኝ እረኞች ናችው፡፡ ነገር ግን የእረኞች አለቃ ይመጣል፤ መንጎቹንም በየስማቸው ይጠራል፤ ይጎበኛቸዋል፤ ስለመንጎቹም ደኅንነት ይመረምራል፡፡ የበጎቹንም እረኞች ከፊቱ ያቆማቸዋል፤ እንደ በደላቸውም መጠን ይከፍላቸዋል፤ እንደሥራቸውም መጠን ይመልስባቸዋል፡፡

መንጎቻቸውን በመልካም ላሰማሩ እረኞች ግን የእረኞች አለቃ ደስ ያሰኛቸዋል፤ ዘለዓለማዊ ሕይወትንና ዕረፍትን ይሰጣቸዋል፡፡ አንተ የማታስተውል ሰነፍ እረኛ ሆይ ሰለመተላለፍህ ቀኝ ክንድህንና ቀኝ ዐይንህን ታጠፋታለህ፡፡ ምክንያቱም ስለበጎቼ የሚሞተው ይሙት፤ የሚጠፋውም ይጥፋ ቅሬታም ካለው ሥጋውን እቀራመተዋለሁ የምትል ሆነሃልና፡፡ ስለዚህም ቀኝ ዐይንህን አጠፋዋለሁ ቀኝ እጅህንም ልምሾ አደርገዋለሁ፡፡ መማለጃን የሚጠብቁትን ዐይኖችህ ይጠፋሉ፤ በጽድቅ የማይፍርደውም እጆችህም የማይጠቅሙ ልሙሾዎች ይሆናሉ፡፡  ብታስተውለው እንደ አንተ በመስኩ ላይ የተሰማሩት በጎቼ የሰዎች ልጆች ናቸው፡፡ እኔ ግን ያንተ ጌታ የሆነኩ አምላክህ ነኝ፡፡ እነሆ በዛ ጊዜ መንጎቼን በለመለመ መስክ በመልካም አሰማራቸዋለሁ፡፡ “መልካም እረኞ ነፍሱን ስለበጎቼ አሳልፎ ይሰጣል፡፡” እንዲሁም “ወደዚህ የማመጣቸው ሌሎች በጎች አሉኝ፡፡ እናም አንድ መንጋ ይሆናሉ፡፡” አንድም እረኛ ይኖራቸዋል፡፡ አባቴ ስለሚያፈቅረኝ ስለበጎቼ ራሴን አሳልፌ እሰጣለሁ፡፡” እንዲሁም “እኔ በር ነኝ ሁሉም በእኔ በርነት ይገባል በእኔም ምክንያት በሕይወት ይኖራል ፡፡ እናም ይወጣል ይገባል ይወጣል ይላል ጌታ፡፡…”