debre_Tsege.jpg

የመነኮሳት አባቶች የጋራ መኖሪያ ቤት ተመረቀ

በደረጀ ትዕዛዙ
 
debre_Tsege.jpgበ ሰሜን ሸዋ ሰላሌ ሀገረ ስብከት በደብር ቅዱስ ደብረ ጽጌ ቅድስት ማርያም ገዳም የተሠራው የአረጋውያን አባቶች መነኮሳት የጋራ መኖሪያ ቤትና መጦሪያ ተመርቆ አገልግሎት መስጠት ጀመረ፡፡መንፈሳዊ ዕውቀት ሀብታቸውን ሲያካፍሉ የኖሩ አባቶችን ለመንከባከብ የተደረገው ጥረት የሚያስመሰግን መሆኑን ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ተናገሩ፡፡
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ በገዳሙ ተገኝተው የመነኮሳቱን መኖሪያ ሕንፃ መርቀዋል፡፡

 

በምእመናን፣ በበጎ አድራጊ ግለሰቦችና ድርጅቶች እንዲሁም በገዳሙ ትብብር ተሠርቶ ጥቅምት 21 ቀን 2003 ዓ. ም ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ እና ሌሎችም ብፁአን አባቶች በተገኙበት ለምረቃ የበቃው ይኸው የጋራ መኖሪያ ቤትና መጦሪያ ከአራት መቶ ሰባ ሺሕ ብር (400,000) በላይ ወጪ የተደረገበት ሲሆን ሃያ (20) አረጋውያን አባቶች መነኮሳትን ለመንከባከብ ያስችላል፡፡

መጦሪያ ቤቱን ባርከው የከፈቱት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ትርያርክ ርዕሰ ሊቀ ጳጳስ ዘ ኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ፕሬዘዳንት፣ የዓለም ሃይማኖቶች ለሰላም የክብር ፕሬዘዳንት እንደተናገሩት፤ «መንሳዊ ዕውቀታቸውን ሲያካፍሉ የኖሩ አባቶች ሲደክሙ ማረፊያና መንከባከቢያ ስፍራ መዘጋጀቱ ተገቢ እና ትውልዱ ሊከተለው የሚገባ ተግባር ነው፡፡» ብለዋል፡፡

ቅዱስ ሲኖዶስ በየጊዜው የሕፃናት ማሳደጊያ፣ የአረጋውያን መጦሪያና የጎልማሶች መማሪያ በየሀገረ ስብከቱ እንዲቋቋም የታዘዘ መሆኑን የጠቀሱት ቅዱስነታቸው፤ ሊቃነ ጳጳሳት ከመንፈሳዊ ልጆቻቸው ጋር በመሆን ይህንኑ ለማከናወን እየጣሩ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ለአረጋውያኑ አስቦ ኮሚቴው የድርሻውን ለመወጣት የሠራው በጎ ሥራ ለሌሎችም አርአያ የሚሆን መሆኑንም አስገንዝበዋል፡፡

የባሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ይስሐቅ በበኩላቸው፤ የደቀ መዛሙርት መገኛ በሆነው በዚህ ስፍራ አባቶች መነኮሳትን አስቦ ይህን በጎ ተግባር መፈጸም ቤተ ክርስቲያኒቱ የምትደግፈው የተባረከ ሥራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

አረጋውያኑ በገዳሙ ለረጅም ዘመን መንፈሳዊ አገልግሎት ሲፈጽሙ የነበሩ መሆኑን ጠቅሰው፤ የተደረገላቸው ድጋፍ የጸሎት ተግባራቸውን ለመቀጠል የሚያስችላቸው በመሆኑ ኮሚቴው ምስጋና ይገባዋል ብለዋል፡፡

የገዳሙ አበምኔት መልአከ ሰላም ቆሞስ አባ ገብረ ሥላሴ መስፍን አስተባባሪ ኮሚቴውን በመወከል ባቀረቡት ሪፖርት፤ በቅዱስነታቸው መልካም ፈቃድና መመሪያ መሠረት ሚያዝያ 30 ቀን 2000 ዓ.ም የተቋቋመው ኮሚቴ ዋነኛ ዓላማው የአረጋውያን አባቶች መነኮሳት መኖሪያ ቤት ማሠራት፣የዕለት ምግባቸውን ማቅረብ እና አጠቃላይ ጤንነታቸውን መንከባከብ ነው፡፡

በዚህ መሰረት ኮሚቴው ተግባሩን በአግባቡ እንደተወጣ የገለጡት አበምኔቱ አረጋውያን አባቶች ቀደም ሲል ያጋጠማቸውን ምግብ የማጣት ችግር ከማቃለል ጎን ለጎን አባቶችን የሚከባከብና ንጽሕናቸውን በመጠበቅ የሚያገለግል ሰው በመመደብ ችግራቸውን ለመፍታት ተችሏል ብለዋል፡፡ በዚህ ተግባርም አሁን በገዳሙ የሚገኙ አገልጋይ መነኮሳት አባቶች የበለጠ ተስፋ አግኝተው መንፈሳዊ አገልግሎታቸውን እንዲፈጽሙ እንዳበረታታቸው መገንዘብ እንደተቻለም አስረድተዋል፡፡

የአረጋውያኑ መጦሪያ ከመኖሪያ ክፍላቸው የመመገቢያ፣ የማብሰያ፣የመታጠቢያ የመፀዳጃ እና አዳራሽን ያካተተ መሆኑን በሪፖርቱ ተመልክቷል፡፡አረጋውያኑ እያንዳንዳቸው የየራሳቸው ክፍል ያላቸው ሲሆን አልጋ፣ ፍራሽ፣አንሶላ፣ ብርድልብስ፣ ጋቢ፣ የሌሊት ልብስ እንዲሁም ለመነኮሳት የሚሆን አልባሳት እንደተሟሉላቸው ተገልጧል፡፡

የገዳሙ አበምኔት አረጋውያኑን ለመደገፍ በተደረገው ጥረት ድጋፋቸውን ላደረጉ ለሀገረ ስብከቱ እና በጎ አድራጊ ምእመናን በልዑል እግዚአብሔር ስም ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

ወደፊትም አረጋውያኑን በገንዘብ ለመደገፍ ለሚሹ የደ/ቅ/ደብረ/ጽጌ ቅ/ማሪያም የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አራት ኪሎ ቅርንጫፍ የባንክ ሒሳብ ቁጥር 0173036575400 ቢልኩ እንደ ሚደርስ ተናግረዋል፡፡

ወደ አረጋውያኑ መጦሪያ የገቡ አንዳንድ መነኮሳት አባቶች በሰጡት አስተያየት በጸሎትና በምስጋና ቀሪ ዕድሜያቸውን እንዲያሳልፉ የተመቸ ቦታ ማግኘታቸው እንዳስደሰታቸውም ተናግረዋል፡፡

የ85 ዓመት ዕድሜ ባለፀጋ የሆኑ አባ ወልደ ትንሳኤ በሰጡት አስተያየት፤በገዳሙ ለሠላሳ ሦስት ዓመታት በቅዳሴ መምህርነት ሲያገለግሉ መኖራቸውን ጠቅሰው ዛሬ በደከማቸው ጊዜ ደጋፊ ማግኘታቸው እጅግ እንዳስደሰታቸው ተናግረዋል፡፡ ሌሎች አባቶችም በተሰጣቸው ክብር እግዚአብሔርን ሲያመሰግኑ፣ለሕዝቡና ለሀገሪቱ ሰላም በመጸለይ እነደሚተጉ ተናግረዋል፡፡

ገዳሙ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ባስልዮስ በ1938ዓ.ም ከተመሠረተ ጀምሮ በርካታ  ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንን ማፍራቱ ይታወቃል፡፡

«በአዳም ምክንያት ሁላችን እንደምንሞት፣ እንዲሁም በክርስቶስ በኲርነት ሁላችን እንነሣለን፡፡» 1ኛ ቆሮ. 15፥22

                            ክፍል አራት

በጸጋ እግዚአብሔር አምላኩ የከበረ ይህ ሐዋርያው ጳውሎስ ትምህርቱን የበለጠ ተቀባይነት ያለው ለማድረግ  ብርሃነ እግዚአብሔር ኦሪትን ለሐዲሱ ምስክር እያደረገ ያስተማምናል፡፡ስለሆነም «ነሥአ መሬተ ወገብሮ ለእጓለ እመሕያው ወነፍሐ ላዕሌሁ መንፈሰ ሕይወት፤እግዚአብሔር አዳምን ከምድር ዐፈርን ወስዶ ፈጠረው፡፡ የሕይወትንም እስትንፋስ አሳደረበት፡፡»ብሎ መጽሐፍ እንደተናገረ በዚች ነፍስ ሕይወትነት የሚኖር ሥጋ አስቀድሞ መፈጠሩን ይገልጽና፤ከትንሳኤ ዘጉባኤ በኋላ ግን መንፈስ ቅዱስ ሕይወት ሆኖት የሚኖር ሥጋ እንደሚገኝ /እንደሚነሳ/ ለአጽንዖተ ነገር ደጋግሞ ይናገራል፡፡ ዘፍ 2÷7

ከዚህም አንጻር «በነፍስ ሕያው ሆኖ የሚኖር ቀዳማዊ አዳም አስቀድሞ ተገኝቶአል፡፡ በመለኮታዊ ሕይወት ሕያው ሆኖ የሚኖረው ዳግማዊ አዳም ክርስቶስ ከአምስት ሽሕ አምስት መቶ ዘመን በኋላ በአዳም ባሕርይ ተገኝቶአል፡፡» ብሎ ቅደም ተከተሉን ከአሳየ በኋላ በትንሳኤ ዘጉባኤ የሚነሳ የመጀመሪያው ሰው የአዳም ዘር ሁሉ መሬታዊ እንደሆነ እንደ ሰማያዊው የባሕርይ አምላክ ክርስቶስም ሰማያዊ እንደሚሆን ያረጋግጣል፡፡በትንሳኤ ዘጉባኤ የሰው ልጅ ሁሉ የሚያገኘውን የተፈጥሮ መዓርግ መሬታዊ አዳም መምሰልን በስሕተቱ፣ በኀጢአትና በሞት ሀብቱ፣ ገንዘቡ እንደ አደረገ ሁሉ፤ ሰማያዊ ክርስቶስ መምሰልንም በዘለዓለም ሕይወትና በጸና ቅድስና ሀብቱ ገንዘቡ ያደርጋል፡፡ እያለ በሙታን ትንሳኤ ጥርጥር ያገኘባቸው የቆሮንቶስ ምእመናን ደቀ መዛሙርቱን ልባቸውን በተስፋ ሕይወት ይመላዋል፡፡ምክንያቱም ተስፋ መንግሥተ ሰማያትን ሥርየተ ኀጢአትን ያገኘ ክርስቲያን ክርስቶስን የሚመስልበት ምስጢር ትንሳኤ ዘጉባኤ ነውና ይህም መንግሥተ እግዚአብሔርን ሀገረ ሕይወትን ለመውረስ በክብርና በቃለ ሕይወት ተጠርቶ የሚቆሙበት ዐደባባይ ዳግም ልደት ነው፡፡ፊል 3÷20-22 ፣እርሱን የሕይወት ባለቤት ክርስቶስን የመምሰል ታላቁ ቁም ነገርና የማያልቅ ጥቅም በእርግጥም ይህ እንደሆነ ከሐዋርያው መልእክተ ቃል እነሆ እንረዳለን፡፡ ይህን ለመረዳትም የዕውቀትና የማስተዋል ባለቤቱ እርሱ መድኃኒታችን ስለሆነ ፈቃዱን በተሰበረ ልቡና ዘወትር መጠየቅ ታላቅ ብልኅነት ነው፡፡

እነሆ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ አንደበተ ርቱዕ ጥዑመ ልሳን ሆኖ በትምህርተ ወንጌል ለደከመላቸው ወገኖች በቁጥር 50ኛ መልእክቱ «ወንድሞቻችን ይህ ሥጋዊ ደማዊ ሰው መንግሥተ ሰማያትን አይወርስምና ይህን አውቄ እነግራችኋለሁ፡፡»በማለት ይህ ሟች፣ ጠፊ ኃላፊ፣ ፈራሽ፣ በስባሽ ሥጋ በመቃብር ታድሶ ካተነሳ ሕያው ማሕየዊ መንፈስ ቅዱስን ገንዘቡ ሀብቱ እንዳያደርግ ያውቁ ዘንድ ሳይታክት ያስገነዝባቸዋል፡፡ ሞት ርስተ አበው ሆኖ ለሁሉ የሚደርሰው ይህ ኃላፊ ጠፊ ሥጋና ደም ተለውጦ የማይጠፋ ሕያው ሆኖ ለትንሳኤ ዘጉባኤ እስኪደርስ ነው ስለሆነም የሞትን ኃይል ኀጢአትን እንጂ ሞትን ሳንፈራ ትንሳኤ ሙታንን በጽኑ ተስፋ መጠበቅ ይገባናል፡፡ቅዱስ ጳውሎስ የትንሳኤን ሁኔታ ሲያስረዳ «ናሁ ኅቡአ ነገረ እነግርክሙ ፤ እነሆ ስውር ረቂቅ ሽሽግ አሁን የማይታወቅ ነገርን እነግራችኋላሁ፤የሰው ልጆች ሁላችንም ሞተን በስብሰን ተልከስክሰን የምንቀር አይደለም፡፡» «ወባሕቱ ኲልነ ንትዌለጥ በምዕር ከመ ቅጽበተ ዐይን በደኀሪ ንፍሐተ ቀርን፤በኋለኛው የዐዋጅ ቃል እንደ ዐይን ጥቅሻ ፈጠነን ከዚህ ተፈጥሮአችን ወደ አዲስነት እንለወጣለን፡፡» ብሎ ከአስታወሰ በኋላ የሦስተኛ ደረጃ ዐዋጅ በተነገረ ጊዜ ሙታን ከቁጥራቸው ሳይጐድሉ፤ አንዲት አካል ሳይጐድላቸው እንደሚነሡ ገልጦ ያስረዳል፡፡ ይህ ሓላፊ ጠፊ ሥጋችን የማይጠፋ የማያልፍ ሆኖ በመለወጥ ማለት ሕያው መንፈስ ቅዱስን ገንዘቡ፣ ሀብቱ በማድረግ ለዘለዓለም ሕይወት ይነሳል ማለት ነው፡፡ይህ ጸጋና በረከት ለሰው የተጠበቀው ጥንቱን ለሕይወት በፈጠረው ቸሩ አምላክ እግዚአብሔር ነው፡፡ ሰው ግን ከሕያውነት ኑሮው ወደ ሞት ጐራ ገብቶ ስለነበር በጥንተ ተፈጥሮ ታድሎት የነበረው በሕይወት መኖር ይመለስለት ዘንድ እግዚአብሔር ወልድ በተለየ ስሙ፣ በተለየ አካሉ፣ በተለየ ግብርና ኩነቱ /አካኋኑ ኹኔታው/ከቅድስት ድንግል ማርያም ተወልዶ ክሶ፣ ሙቶና ተቀብሮ በመነሳት እነሆ የዘለዓለም ሕይወትን በትንሳኤ ዘጉባኤ ያድለዋል፡፡

ትምህርቱን አጠናክሮ ለመፈጸም በተገለጠው ምዕ.በቁ. 54 ላይ «ወአመ ለብሰ ዝንቱ መዋቲ ዘኢይመውት፤ ይህ ሟች የሆነ ሥጋ ከትንሳኤ በኋላ ተለውጦ የተነሳ የማይሞት የሆነውን ሥጋ በለበሰ ጊዜ» ከአለ በኋላ እነሆ! ሞት በመሸነፍ ባሕር ጠለቀ ሰጠመ ተብሎ በልዑለ ቃል ነቢይ የተነገረው ቃል ይፈጸማል፣ይደርሳል፡፡ ይህም ሞት ሆይ ድል መንሳትህ ወዴት አለ? መቃብርስ ብትሆን ሰውን ይዘህ ማስቀረትህ ወዴት ነው? አለ የሞትም ኀይሉ ብርታቱ ኀጢአት ሲሆን፣ የኀጢአትም አበረታች ትእዛዛተ ኦሪት ናቸው፡፡ አለ፡፡ ኀጢአት፣ ኀጢአትነቱ የታወቀው በሕገ ኦሪት ደጉ ከክፋው፣ ክፉውም ከደጉ ተለይቶ በመደንገጉ፣ በመገለጡ መሆኑን ሲያመለክት ነው፡፡ ምንጊዜም ሕግ ሥርዐት መውጣቱ በተላላፊው ወገን ላይ የጥፋት ነጥብን አስቆጥሮ ፍርድን ሊያስከትል፣ ከፍርድ በኋላም ቅጣትን ለማምጣት እንደሆነ ይህች ሕግ ልኩንና ተጨባጭ ማሰረጃን አፍሳ በነሲብ ስለምትሰጠን ለልቡናችን ይደምንብናል ማለት አይቻልም፡፡ዕውቅ ነው፡፡ ኢሳ 25÷8፣ ሆሴ 13÷14፣ሮሜ 13÷19 እንዲህ ስለተደረገለን ፣ እንዲህም ስለሚደረግልን «ወለእግዚአብሔር አኮቴት ዘወሀበነ ንማዕ በእግዚእነ ኢየሱስ ክርስቶስ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቤዛነት ከሰው ምክንያት ይኸው እንግዲህ በርኅርኅት ሕገ ወንጌል ኦሪትን፣ በጽድቅ በእውነተኛ ንስሐ ኀጢአትን፣በትንሳኤ ሞትን ድል እንነሳ ዘንድ ድል ማድረጉን የሰጠን ሁሉን ያዥ ሁሉን ገዥ እግዚአብሔር አምላክ ይክበር ይመስገን፡፡»በማለት የምግበ መላእክት ስብሐተ እግዚአብሔር ፍጹም ተሳታፊነቱን አንጸባርቆ ገለጠው፡፡በመልእክቱ ማጠቃለይም «እርስ በርሳችሁ የምትዋደዱ እግዚአብሔርን የምትወዱ እርሱም የሚወዳችሁ ወንድሞቻችን ሆይ! ብርቱዎች ሁኑ፤ በማናቸውም ሥራ ሁሉ ዝግጁዎች ሁኑ»ብሎ ሲያበቃ ከላይ እንደታተተው፣እንደተዘረዘረው ከሃይማኖታቸው እንዳይናወጡ፣ እግዚአብሔርን ለማገልገል፣ ሁልጊዜ ከሕጋዊው ሥራ ላይ የትሩፋት ሥራን አብዝተው እንዲሠሩ የትንሳኤ ሙታን ደገኛ የክብር የዋጋ የጽድቅ ማግኛውን ምስጢር ገልጦ ያስረዳቸዋል፡፡»ይልቁንም በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ከማመናቸው የተነሳ የተቀበሉት መከራ ሁሉ ከገለጠላቸውና ከአረጋገጠ በኋላ በሃይማኖታቸው መሠረትነት የጽድቅ መልካም ሥራን አብዝተው እንዲሠሩና ለክብር ትንሳኤ እንዲበቁ እንዲዘጋጁም በፈሊጥ ከልቡ ይመክራቸዋል፣ያስተምራቸዋል፤ ያንጻቸዋል፡፡ 2ኛ ዜና መዋ 15÷7 ፣2ኛ ጴጥ 1÷5፡፡ለባስያነ ኀይለ እግዚአብሔር /የእግዚአብሔር ኀይሉን እንደሸማ የተጐናጸፋችሁ/ ክርስቲያኖች ሆይ! አክሊለ መዋዕ የድል አክሊል ሀብተ መንፈስ ቅዱስን የተቀዳጀው ሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስ በቆሮንቶስ ሰዎች አንጻር እንዳስገነዘበን «በአዳም በደል ምክንያት ሁላችን እንደምንሞት፣ እንዲሁም በክርስቶስ ካሳና በኩርነት ሁላችንም እንነሳለን፡፡»በሚል ርእስ «ርእሱ ለአእምሮ፤ የዕውቀት መገኛዋ»የሆነ መድኅነ ዓለም ክርስቶስ በማይመጠን ቸርነቱ በገለጠልን መጠን የምስጢረ ትንሳኤን እሙንነት ይኸው አብራርተን አቅርበናል፡፡ ተስፋው እንደሚፈጸም አምኖ ለመጠባበቅ በርትቶ በማስተዋል ደጋግሞ ማንበቡ ግን የእናንተ ፈንታ ይሆናል፡፡በመሆኑም የሙታን ትንሳኤ መነሳት ወይም አነሳሥ ለተለየ አዲስ ሕይወት ነው፡፡ በዓለመ ሥጋ ምንም ምን አይመስለውም፡፡ይህንም ራሱ ባለቤቱ መድኀኒታችን በዘመነ ሥጋዌው «ወአመሰ የሐይው ምውታን ኢያወስቡ፣ወኢይትዋሰቡ፣ አላ ከመ መላእክተ እግዚአብሔር በሰማያት እሙንቱ፣ ሙታንስ በሚነሡበት ጊዜ አያገቡም፤ አይጋቡም፤ እነርሱ በሰማያት እንደ እግዚአብሔር መላእክት ሆነው ይኖራሉ እንጂ፡፡»በማለት በሕያው ቃሉ የሰጠው ትምህርት በግልጥ ያስረዳናል፡፡ በጌታችን መዋዕለ ሥጋዌ የነበሩ የእምነት መሪዎች፤ በዘመናችንም ብጤዎቻቸው «ሙታን ከተነሡ በኋላ ለዘለዓለም አግብተው እንደሚኖሩ በመስበክ እያስጐመጁ ለያዙት ሃይማኖት ማስፋፊያ አድርገውት ይገኛል፡፡ ይህን አጉልና ከንቱ ሽንገላ ለይቶ በማወቅ ወደ ዕውነት መመለስ፣ ጸንቶ መኖርም በመንፈስ ቅዱስ መቃኘት ነው፡፡ 2ኛ ቆሮ 11÷13-16 ኤፌ 5÷6 ከትንሳኤ ዘጉባኤ በኋላ መብላት መጠጣት የመሳሰለው ሰብአዊ ግብር የለም ጌታችን ከትንሳኤው በኋላ በቅዱሳን ሐዋርያት ፊት የበላው ምግብ አስፈልጐት አይደለም በምትሐት ነው ብለው እንዳይጠራጠሩና ትንሳኤውን እንዲያምኑ ማስረጃ ይሆናቸው ዘንድ ነው፡፡ሉቃ 24÷14-44

መላልሰን እንዳስገነዘብነው ትንሳኤ ዘጉባኤ የክብር የሚሆነው ከዳግም ዘለዓለማዊ ሞት የዳኑ እንደሆነ ብቻ መሆኑ የሚካድ አይደለም፡፡ይህም ዳግም ሞት የሰው ከእግዚአብሔር መለየት እንደሆነ ይታወቃል፡፡ በመጽሐፈ አበው «ሞታ ለነፍስ ርኂቅ እም እግዚአብሔር ፤ የነፍስ ሞቷ ከእግዚአብሔር መለየቷ ነው፡፡» እንደተባለው ነው፡፡

በአስተዋይ ልቡና ሊተኮርበት የሚገባው ምን ጊዜም የሕይወት ባለቤት እግዚአብሔር የባሕርይ ጐዳናው ምሕረትና ቸርነት ብቻ እንደ ሆነ ከምእመናን ንጹሕ ልብ ሊደበቅ አይገባውም፡፡መዝ 24÷10 የክብር ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስም ትንሳኤውን ለመላው ዓለም አብርቶ የገለጠው የሰው ሁሉ ትንሳኤ ያለጥርጥር የታወቀ የተረዳ ይሆን ዘንድ ነው፡፡ ግበ.ሐ. 26÷23

ከላይ በመልእክቱ ማእከል እንደተገለጸው በሰው ሁሉ አባት በአዳም በደል የሰው ልጅ በሙሉ ሞተ፡፡ በእርሱ በባሕርይ አምላክ ክርስቶስ ሰው ሆኖ ካሰ እነሆ! መላው የሰው ልጅ ከሞት ከመርገም ዳነ፡፡ የጌታችን ካሳ የራሱ አለማመን ከሚገድበው በስተቀር ማንንም ከማን አይለይም፡፡ዮሐ 3÷36፤ 5÷24 ሮሜ 5÷12-19 በጌታችን ምስጢረ ሥጋዌና ነገረ አድኅኖት አምኖ መጠመቅ ከእርሱ ጋር ተቀብሮ የመነሳት ምስጢር ነው፡፡የትንሳኤ ሙታንም ምልክት ይሆናል፡፡መድኃኒታችንን አምነው ለተቀበሉት ዋጋቸው የሆነ ልጅነትን ይሰጣቸዋል፡፡ በልጅነታቸውም እርሱ እንደተነሳበት ባለ ሥልጣኑ ትንሳኤ ዘለክብርን ያስነሳቸዋል፡፡ በትንሳኤያቸውም የዘለዓለም መንግሥቱ ሀገረ ሕይወትን ያወርሳቸዋል፡፡ ዮሐ. 1÷13፣ ሮሜ 1÷5፡፡

ይህን የትንሳኤ ሙታን ተስፋ ለሰው ሁሉ ተግቶ ያለፍርሃት መመስከር ክርስቲያናዊ ግዳጅ ነውና አምነን በማሳመኑ ሥራ ልንበረታ ይገባናል፡፡ሲራ 4÷20-29፣ 1ኛ ተሰ 4÷18

በገነት በመንግሥተ ሰማያት የማይሰለች ተድላ ደስታ እንጂ ሐዘንና መከራ የለም፡፡ኢሳ 49÷10

ይህን ታላቅ ምስጢር ዐውቀን በሕያው ቃሉ መመራት በእጅጉ ይገባናል፡፡ይህንም በልቡናችን፣ ከመምህራነ ወንጌል፣ ከቅዱሳት መጻሕፍት ተምረን ተመራምረን አምነን ለትንሳኤ ዘለክብር እንድንበቃ በቸርነቱ ይርዳን፡፡

የኅዳር ጽዮን በዓል አከባበር ዛሬም ቀጥሎ በድምቀት ተከብሯል።

ዲ/ን አሉላ መብራቱና በተ/ሥላሴ ጸጋ ኪሮስ

ኅዳር 20 ቀን ከዋዜማው ጀምሮ መከበር የጀመረው የኅዳር ጽዮን በዓል ዛሬም ቀጥሎ በድምቀት ተከብሮ ውሏል።

ከትናንትና ማታ 2፡00 ደወል ከተደወለበት ጀምሮ፥ ሊቃውንት ካህናትና ዲያቆናት  ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት በተገኙበት በስብሐተ ማኅሌት በማድረስ ሌሊቱን አሳልፈዋል።

ሥርዓተ ማኅሌት እንዳለቀ ዛሬ ጠዋት 1፡00 ዑደተ ታቦት ተጀምሯል። ሁለት ዓይነት ዑደት የተካሄደ ሲሆን የመጀመሪያው ዑደት በሐውልት አደባባይ ተደርጓል። በዚያም የአክሱም ሊቃውንትና የሰ/ት/ቤት መዘምራን የክብረ በዓሉን ዝማሬ አቅርበዋል። በቦታው ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል፥ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ትምህርተ ወንጌል ሰጥተዋል።

ሁለተኛው ዑደት ቅዱስ ያሬድ የአርያም ዜማውን ባሰማበት በሙራደ ቃል ተከናውኗል። በዚህኛው ዑደት፥ ቅዱስነታቸው አቡነ ጳውሎስ ሠፋ ያለ ትምህርተ ወንጌል በሁለት ቋንቋ በአማርኛና በእንግሊዝኛ ሰጥተዋል። የማዕከላዊ ትግራይ አክሱም ሃገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ሰላማ በዓሉን በተመለከተ አጠር ያለ መግለጫ ሠጥተዋል። በቅዱስነታቸው ጋባዥነት ብፁዕ አቡነ ኤልሣዕ ተጨማሪ ትምህርት ያስተማሩ ሲሆን የትግራይ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አባይ ወልዱ በበኩላቸው እለቱን አስመልክተው በንባብ ንግግር አሰምተዋል።

ሥርዓተ ቅዳሴ የተጀመረው ከቀኑ 6፡20 ነበር። በእለቱ ሠራየ ዲያቆን ሆኖ የቀደሱትና ከማኅበረ ቅዱሳን የአማርኛ መካነ ድር ጋር የስልክ ቆይታ ያደረጉት መ/ር ፍስሐ ጽዮን ደሞዝ እንደገለጹልን፥ በብፁዕ አቡነ ገሪማ፥ በብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስና በብፁዕ አቡነ ዲሜጥሮስ የተመራው የቅዳሴ ሥርዓት በ3 መንበር የተከናወነ ሲሆን፥ ሥርዓተ ቁርባኑ በእያንዳንዳቸው በ3 አቅጣጫ በአጠቃላይ በ9 ሙሉ ቀዳሽ ተከናውኗል። የቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ የጠጠር መጣያ ቦታ እስከሚታጣ ሙሉ ነበር።
እንደ መ/ር ፍስሐ ጽዮን ገለጻ፥ እርሳቸው በቀደሱበት በዋናው የእመቤታችን ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የነበሩት መላው ምእመናን የቅዱስ ሥጋውና የክቡር ደሙ ተሳታፊ መሆናቸው ልዩ ድባብ ፈጥሯል። በአጠቃላይ ለምእመናን ቅዱስ ቁርባን ለማቀበል ብቻ ወደ አንድ ሰአት የሚጠጋ ክፍለ ጊዜ እንደወሰደ አያይዘው ገልጸውልናል።
ከዋዜማው ጀምሮ በ100,000ዎች ለሚገመቱ ምእመናን በአራቱም አቅጣጫ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ሲስጥ ውሏል።  

/ከትናንት ጀምሮ መረጃዎችን ሲያደርሱን ለነበሩና ለተባበሩን ለንቡረ እድ በላይ መረሳ፣ ለመ/ር ፍስሐ ጽዮን ደሞዝና ለመ/ር ዲበኩሉ ልሳነ ወርቅ በእግዚአብሔር ስም ምስጋናችንን እያቀረብን ጥንቅራችን በዚህ እንቋጫለን/

        
metshafe_bilhat.jpg

የአዳዲስ ፈጠራ ግኝቶች ማበረታቻ የሽልማት ፕሮጀክት ትግበራ ተጀመረ።

በተ/ሥላሴ ጸጋ ኪሮስ
 
metshafe_bilhat.jpgየሙያ አገልግሎትና አቅም ማጎልበቻ ዋና ክፍል የአዳዲስ ፈጠራ ግኝቶች ማበረታቻ የሽልማት ፕሮጀክት ትግበራ ጀመረ። በፕሮጀክቱ ትውውቅ መርሐ ግብር ላይ ለትግበራ መነሻ ይሆናል የተባለው «መጽሐፈ ብልሃትም» ተገምግሟል።
 
ፕሮጀክቱ ማኅበረ ቅዱሳንና ኢንጅነር ሙሉጌታ ዘርፉ በተፈራረሙት የመግባቢያ ሠነድ መሠረት ፈጠራንና መልካም የሆነውን የቴክኖሎጂ ሽግግር ማበረታት፥ ቤተ ክርስቲያንን፣ ትውልድን ፣ ሀገርን የሚጠቅም አቅም ለማሳደግ አስተዋጽኦ ማድረግ እንደሆነ በመርሐ ግብሩ ትውውቅ ወቅት የተበተነው ወረቀት ያስረዳል፡፡
መርሐ ግብሩን ያዘጋጀው የማኅበረ ቅዱሳን የሙያ አገልግሎትና አቅም ማጎልበቻ ዋና ክፍል ሲሆን በፕሮጀክት ትውውቅ መርሃ ግብር ላይ የክፍሉ ሓላፊ ዶ/ር ሣሙኤል ኃ/ማርያም እንደተናገሩት ከሆነ የፕሮጀክቱ ዋነኛ ዓላማ በሁሉም የዕድሜ ክልል ያሉ ኢትዮጵያዊያን ሁሉ በየደረጃቸው መስራትና የፈጠራ ባለቤት የሚሆኑበትን መንገድ ማሳየት ነው፡፡ በግኝቱ ውስጥ ለሚያሸንፋ ግለሰቦች ሽልማቶችን በመስጠት ፈጠራን ያበረታታል በተጨማሪም ያለብንን የተለያዩ ችግሮች በሙያ በማገልገል በተሰጠን መክሊት አትርፈንባቸው ገብርሄር ተብለን ሰማያዊ ሽልማት እንድናገኝ ነው፡፡

በትውውቅ መርሐ ግብሩ ላይ የተገኙትም የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ስዩም እንደገለጹት ማኅበሩ ይህንን ፕሮጀክት ለተጠቃሚ ለማድረስ ሲወስን ከዘርፉ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ቤተ ክርስቲያንንና ሀገሩን በአካባቢያው ከሚያገኛቸው ቁሳቁሶች በማዘጋጀት እንዲጠቀም ነው፡፡ በዚህ በኩል ሁላችንም የድርሻችንን እና የሚጠበቅብንን ሁሉ ማድረግ ይገባናል ብለዋል፡፡

በመርሐ ግብሩ ላይ ለፕሮጀክቱ ትግበራ መነሻ ይሆናል የተባለውና በኢ/ር ሙሉጌታ ዘርፉ የተዘጋጀው መጽሐፈ ብልሃት አንደኛ መጽሐፍም ተገምግሟል፡፡ መጽሐፉ በ24 ክፍሎችና በ92 ገጾች በምርምርና ሥርዐት የተዋቀረ መሆኑን ዶ/ር ኢ/ር ብርሃኑ ይግዛው የግምገማ ግብረ መልስ /Feed back/ ሲያቀርቡ ገልጸዋል፡፡

ገምጋሚው መጽሐፉ የተጻፈበትን ሥርዓትና ስልት ሲገልጹ፥ ሥልጣኔ የሚፈጥሩት እንጂ የሚቀበሉት ነገር ያለመሆኑን ያመሰጠረ መጽሐፍ ነው ብለው፥ በይዞታቸው ጥንታዊ ግኝቶች፣ በአቀራረብ ስልታቸው ግን አዲስ ሊባሉ የሚችሉ እሳቤዎችን፣ ምን አልባትም በቴክኖሎጂ ዘርፍ ገና ያልተፈለሰፉ ግን ሊተገበሩ የሚችሉ ድንቅ ሀሳቦችንም እያዋዛ የሚያቀርብ መጽሐፍ ነው ብለዋል፡፡   

ስለ መጽሐፉ ጠቀሜታ በዘረዘሩበት የግምገማቸው አካል ምርምርና ሥርፀት ምን ሊሆን እንደሚችል የሚያስረዳና፥ እያንዳንዱ ሰው የፈጠራ ችሎታን በተመለከተ እንዲማር የሚያደርግ ነው፡፡ እኒህም የመጠቁ ቤተ ሙከራዎችን በማይጠይቅ ሁኔታ ነው ብለዋል፡፡

ዶ/ር ኢ/ር ብርሃኑ በማጠቃለያ ሀሳባቸው መጽሐፉ ጥቂት ሊያካትታቸው ስለሚገቡ ነገሮች ጠቅሰው፥ ይህ በጎ ጀማሮ በየት/ቤቱ፣ በቤተሙከራዎች እንዲሁም በፋብሪካዎች ተሠራጭቶ በዚህ ረገድ ሁሉም የኢትዮጵያ ክልሎች ይሄው በጎ የቴክኖሎጂ መሠረታዊ ሀሳብ የሚስፋፋበትን መንገድ በመቀየስ የበኩላቸውን ጥረት ማድረግ እንዳለባቸው አሳስበዋል፡፡

የማ/ቅዱሳን ሙያ አገልግሎትና አቅም ማጐልበቻ ዋና ክፍል ማኅበሩ ከተነሣለት ቤ/ክንን በሙያ በእውቀትና በገንዘብና በጉልበት ለማገልገል ካለው ዓላማ አንፃር የቤ/ክንን ልጆች በሙያ አገልግሎት ለማሣተፍ የተቋቋመ ክፍል ነው፡፡
     
   

Kepilatos_Adebabay_Eske_Litostra.JPG

ከጲላጦስ ዐደባባይ እስከ ሊቶስጥራ

Kepilatos_Adebabay_Eske_Litostra.JPG

ሀብዎሙ ዘይበልዑ/ክፍል ሁለት/

 የሚበሉትን ስጡአቸው /ማቴ. 14፣16 /

  በመ/ር አፈወርቅ ወ/አረጋዊ

ባለፈው ትምህርታችን «የሚበሉትን ስጡአቸው» በሚል ርእስ ቅዱሳን ሐዋርያት ለጌታችን ያቀረቡትን ጥያቄ፣ ጌታችን የመለሰላቸውን ድንቅ ነገር የሕብስቱ መባረክና መበርከትን በተመለከተ ማስነበባችን ይታወሳል፡፡ በዚህ እትም ደግሞ ካለፈው የቀጠለውን አቅርበናልና መልካም የሕይወትና የድኅነት ትምህርት ያድርግልን፡፡

በሊቀ ነቢያት ሙሴ መሪነት ወደ ምድረ ርስት ይጓዙ ለነበሩት ሕዝበ እስራኤል እግዚአብሔር እንዲህ አላቸው፡፡ «በሥርዓቴ ብትሔዱ ትእዛዛቴንም ብትጠብቁ ብታደርጉትም ዝናባችሁን በወቅቱ አዘንባለሁ፤ ምድሪቱም እህሏን ትሰጣለች፤ የሜዳውም ዛፎች ፍሬያቸውን ይሰጣሉ፤ የእህሉም ማበራየት በእናንተ ዘንድ እስከ ወይኑ መቆረጥ ይደርሳል፤ የወይኑ መቆረጥም እስከ እህሉ መዝራት ይደርሳል፤ እስክትጠግቡም ድረስ እንጀራን ትበላላችሁ. . .» ዘሌዋ. 26፣3-13፣ ዘዳ. 11፣13-17፡፡

 

በዚህ ርእሰ ትምህርት ላይ በትኩረት የምንመለከታቸው ዐበይት ነጥቦች የሚከተሉት ናቸው፡፡

ሀ/ የእግዚአብሔርን ርኅራኄ፣ ቸርነትና መግቦት
ለ/ በመታዘዝ የሚገኘውን ታላቅ በረከት
ሐ/ ለጋስነትን
መ/ የችግር ተካፋይ መሆንን
ሠ/ ያለውን ማካፈልን
ረ/ የሥራ ድርሻን ማወቅ
 

በአጭሩ ለመረዳት ያህል እነዚህን አጉልተን ጠቀስን እንጂ፤ በዚህ ዐረፍተ ነገር ውስጥ እጅግ በርካታ ምስጢራት፣ ትምህርቶችና ትርጓሜዎች አሉ፡፡ ያቀረብናቸውን ነጥቦች በዝርዝር እንመልከት፡፡

መታዘዝ

የተራበውን ሕዝብ እንዲመግቡ ከጌታ የታዘዙት ደቀ መዛሙርቱ /ሐዋርያት/ ዓለምን በምግበ ሥጋ በምግበ ነፍስ እንዲጎበኙት ታዘዋል፡፡ ይህ ብቻ አይደለም እንዲጠብቁት እንዲከባከቡት ቢታመም በተሰጣቸው ሥልጣን እንዲፈውሱት ሙሉ ሥልጣን ተሰጥቶአቸዋል፡፡ መታዘዝንም አስተምሮአቸዋል፡፡

ዓለም ይህን አውቆ ወደ መጋቢዎቹ ወደ ጠባቂዎቹ ቀርቦ ምግበ ሥጋውን ምግበ ነፍሱን ሊመገብ ይገባዋል፡፡ ከሚደርስበት መከራም ሊጠበቅና ሊፈወስ ይችል ዘንድ ወደ ጠባቂዎቹ ካህናት /ሐዋርያት/ በመቅረብ ጠባቂዎቹን አውቆ ከሌላው ሊሸሽ ግድ ነው፡፡ ይህ ሥርዓት ከመታዘዝ አንዱ ነውና፡፡

አበው ነቢያትና ሐዋርያት ለእውነት በመታዘዛቸው ጥቂቱን በማበርከት፣ መራራውን በማጣፈጥ፣ አስገራሚ ተአምራት በማድረግ፣ በጸሎታቸው የሕዝቡን ችግር አስወግደዋል፡፡
1. ነቢየ እግዚአብሔር ኤልያስ ለስራፕታዋ መበለት ትንሿን ዱቄት በማበርከት
2. ነቢየ እግዚአብሔር ኤልሳዕ ልጆቿ በዕዳ የተያዙባትን ሴት ጥቂቱን ዘይት በማብዛት፣ መካን ለነበረችው የሱነማይቱ ሴት ልጅ በመስጠት የአባትነት ድርሻቸውን ተወጥተዋል፡፡

ይህ ሁሉ ሊሆን የቻለው ነቢያቱም ሆነ ሐዋርያቱ በመጀመሪያ ታዛዦች ሆነው በመገኘታቸው ነው፡፡

የሚታዘዝ ይባረካል የማይታዘዝ ደግሞ ይረገማል፡፡ ሰው ለእግዚአብሔር ቢታዘዝ በረከትን ይቀበላል መርገሙ ከእርሱ ይርቃል፡፡

«እሺ ብትሉ ለእኔም ብትታዘዙ የምድርን በረከት ትበላላችሁ፤ እንቢ ብትሉ ግን ብታምፁ ሰይፍ ይበላችኋል፤ የእግዚአብሔር አፍ ይህን ተናግሯልና» ኢሳ. 1፣19፣ ዘዳ. 11፣27፡፡

ምግባራትን ሁሉ መታዘዝ ይቀድማቸዋል በክርስትናው ዓለም መታዘዝ ማለት፤

– ለእግዚአብሔርና ለሕጉ
– ለወላጅና ለቤተሰብ
– ለአካባቢና ለጎረቤት
– እግዚአብሔር ለሾማቸው ካህናት
– በዕድሜ ለገፉ አባቶችና እናቶች

እንደ አስፈላጊነቱ መታዘዝ ይገባል፡፡ ሐዋርያት በቅንነት በመታዘዛቸው በሥራቸው ፍሬ አፍርተዋል፡፡ የሐዋ. 10፣33፡፡

ደቀ መዛሙርቱ ጌታችን ተከተሉኝ ሲላቸው ተከተሉት፡፡ ለሕዝቡ የሚበሉትን ስጡአቸው ሲላቸው ያላቸውን ያለንፍገት በማቅረብ  ሰጡ፡፡

ከእግዚአብሔር የመጣውን ትእዛዝ ሳንጠራጠር ሳንሟገት ጠቃሚ መሆኑን አውቀን በጽኑ እምነት ልንቀበል ያስፈልጋል፡፡

ሰማዕታት በእሳት፣ በስለት፣ በሰንሰለት በጅራፍ፣ በመገረፍ፣ በመስቀል በመሰቀል ይህንና ይህን በመሳሰለው መከራ ተፈትነው በሃይማኖታቸው ጸንተው ፈተናውን ድል አድርገው የተቀበሉትን ቃል ኪዳን ሳይጠራጠሩ መቀበል መታዘዝ ነው፡፡

ለጋስነት

ለጋስ ማለት ያልቅብኛል ይጎልብኛል ሳይል ሳይሳሳ በንፍገት ሳይሆን በቸርነት የሚሰጥ፤ ዘመድ ወገን ሳይል የሰው ወገን የሆነውን ሁሉ የሚረዳ፤ ለተራበው የሚያበላ፣ ለተጠማው የሚያጠጣ፣ ለተራቆተው የሚያለብስ ደግ ቸር የሆነ ሁሉ ለጋስ ይባላል፡፡

በዘመነ አበው በለጋስነት ከታወቁት አባቶች ታላቁን አብርሃምን ብንመለከት በየዕለቱ እንግዳ ይቀበል ነበር፡፡ በዚህ ግብሩም ታላቅ የበረከት አባት እንደሆነ ተነግሮለታል፡፡ ዘፍ. 12፣2፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም «የወንድማማቾች መዋደድ ይኑር እንግዶችን መቀበል አትርሱ በዚህ አንዳንዶች ሳያውቁ መላእክትን በእንግድነት ተቀብለዋል» ዕብ.13፣1-2 በማለት በቸርነት በለጋስነት የተገኘውን ረድኤት በረከት አሳይቷል፡፡

እግዚአብሔር በሀብት በዕውቀት በመግቦት የጎበኛቸው ሁሉ ለጋሶች፣ ሳይነፍጉ ሀብታቸውን፣ ጉልበታቸውን፣ ዕውቀታቸውን፣ ገንዘባቸውን፣ ታማኝነታቸውን የሚሰጡ እንዲሆኑ ይህ ርእሰ ትምህርት ይናገራል፡፡ የሐዋርያት ለጋስነት ከብዙ ነገር ላይ ተነሥቶ ሳይሆን በትንሹ ላይ በመለገስ ለበረከት መብቃትን ያሳያል፡፡

ችግርን መጋራት

በዚች ምድር ላይ የተፈጠረ ፍጥረት ሁሉ በተለይም የሰው ልጅ ችግሩ ይለያይ እንጂ ችግር የማይደርስበት የለም፡፡

አንዱ የገንዘብ ችግር ባይኖርበት የጤና ችግር ይኖርበታል፡፡ በአንፃሩ ደግሞ ገንዘብና ጤንነት ተሟልተውለት በትዳር የሚቸገር፣ ትዳር ተሟልቶለት በልጅ እጦት የሚቸገር ሊኖር ይችላል፡፡ በዚህ በኩል የሚመጣውን ችግር መወጣት ያዳግተዋል፡፡ ጠቅለል ባለ መልኩ ስንመለከት ችግር ዘርፈ ብዙ ነው፡፡ ሁሉንም እንደየችግሩ ልንረዳና ልንረዳዳ፣ በችግሩ ልንጋራ፣ በእጅጉ ያስፈልጋል፡፡ ጠቢቡ ሰሎሞን ወደ ሰርግ ቤት ከመሔድ ይልቅ ወደ ልቅሶ ቤት መሔድ ይሻላል ያለው፤ የተቸገሩትን መርዳት ያዘኑትን ማጽናናት ማረጋጋትን ሲያስረዳን ነው፡፡

የሐዋርያት ጥያቄ የጌታችንም መልስ በችግርና በችግረኞች ላይ የተደረገ ውይይትና መፍትሔም የታየበት ነበር፡፡ የመፍትሔው አካላት ለመሆን ፈቃደኞች እንሁን፡፡ 

ሐዋርያው «በአሁኑ ዘመን ባለጠጎች የሆኑትን መልካም እንዲያደርጉ በበጎ ሥራ ባለጠጎች እንዲሆኑ ሊረዱና ሊያካፍሉም የተዘጋጁ እንዲሆኑ ምከራቸው» 1ጢሞ. 6፣17-19 ይላል፡፡ መርዳት የሚችሉ አካላት በመርዳታቸው የችግር ተካፋዮች መሆናቸውን ማመን ያስፈልጋል፡፡

ድርሻን ማወቅ

ከትንሽ እስከ ትልቅ ከአገልጋይ እስከ ተገልጋይ ከመጋቢ እስከ ተመጋቢ ያለው የሥራ ድርሻውን ማወቅ በእጅጉ  ጠቃሚ ነው፡፡ የሥራን ድርሻ ሳያውቁ መንቀሳቀስ ፍምን በእጅ ጨብጦ አልቃጠልም እንደማለት ነው፡፡ ጆሮ የዓይንን እግር የእጅን ሥራ ሊሠራ እንደማይችል ሁሉ የሥራ ድርሻውን የማያውቅ እንዲሁ ነው፡፡

ዳታንና አቤሮን በሊቀ ነቢያት ሙሴና በሊቀ ካህናት አሮን የሥራ ድርሻ ውስጥ በመግባት ክህነታዊ ሥራ እንሠራለን ብለው አደጋ ላይ ወድቀዋል፤ በእሳት ተበልተዋል፤ ምድር ተከፍታ ውጣቸዋለች፡፡

ንጉሡ ግዝያንም በማን አለብኝነት ተነሣሥቶ በሥጋዊ ሥልጣኑ ተመክቶ ክህነታዊ ሥራ እሠራለሁ በማለቱ በለምጽ ተመትቶ ሞቷል፡፡

የሐዋርያት ድርሻ የሕዝቡን ችግር ወደ ፈጣሪያቸው ማቅረብ፣ የታዘዙትን በቅንነት መፈጸም፣ ያላቸውን ይዘው መቅረብ ነበር፡፡ የጌታችን ድርሻ ለሐዋርያት መመሪያ መስጠት፣ የቀረበውን ማበርከት፣ የተቸገረው ሕዝብ ከችግሩ እንዲላቀቅ ሐዋርያት ድርሻቸውን እንዲወጡ ማድረግ ነበር፡፡ ይህ ችግር ፈች አሠራር ለባለ ድርሻዎች ሁሉ አርአያነት አለው፡፡

በአጠቃላይ በየትኛውም የሥራና የአገልግሎት ድርሻ ሆነን ሕዝብን እንደምናገለግል በቅድሚያ ማወቅ ይኖርብናል፡፡ «የሚያስተምር ቢሆን በማስተማሩ ይትጋ፤ የሚመክርም ቢሆን በመምከሩ ይትጋ የሚሰጥ በልግስና ይስጥ፤ የሚገዛ በትጋት ይግዛ፤ የሚምር በደስታ ይማር» ሮሜ. 12፣7-8 ተብሎ ተጽፏል፡፡

«ሀብዎሙ ዘይበልዑ፤ የሚበሉትን ስጡአቸው» የተባሉ እነማን ናቸው? ለምን ተባሉ? መመሪያውንስ እንዴት ተወጡት? አሁን ከእኛ ምን ይጠበቃል? እንወያይበት፡፡

የሚመግብ ሆነ የሚመገብ ድርሻውን አውቆ ይሥራ፡፡ እንደተሰጠው ልዩ ልዩ ጸጋ መጋቢውም ተመጋቢውም ራሱን አሳልፎ ለፈጣሪው ይስጥ፡፡ መጋቢም ተመጋቢም የምግባቸው ዐውደ ማዕድ፤ ሲሳዮሙ ለቅዱሳን፤ የተባለ   እግዚአብሔር መሆኑን አምኖ መቀበል ብስለት ነው፡፡

የምንመገበውንና የሚመግቡንን ያዘዘልንና የሰጠን እግዚአብሔር ይመስገን አሜን፡፡

አለማመኔን እርዳው

በመ/ር ኃይለማርያም ላቀው

«እምነት፣ ተስፋ ስለምናደርገው ነገር የሚያስረዳ ነው» ዕብ. 11፣1፡፡ የሰው ልጅ ተስፈኛ ወይም ተስፋ ያለው ፍጡር ነው፡፡ አዳም ቢበድልም እንኳን ቸሩ አምላክ በኋላ ዘመን ከልጅ ልጁ ተወልዶ እንደሚያድነው ተስፋ ሰጥቶታል፡፡ አዳምም የመዳኑን ነገር በእምነት ተስፋ በማድረጉ በጊዜው አግኝቶታል፡፡ እምነት ለእግዚአብሔር ያለንን ፍቅር የምንገልጥበት፣ እርሱን ደስ የምናሰኝበት የሕይወት መሠረት ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እምነት እግዚአብሔርን ደስ የምናሰኝበት ጥበብ መሆኑን ሲያስረዳ «ያለ እምነት እግዚአብሔርን ደስ ማሰኘት አይ ቻልም» ብሏል፡፡ ዕብ. 11፣6፡፡

በዘመነ ብሉይ የነበሩ በእምነት ጥን ካሬአቸው የተመሰከረላቸው አበውና እመው በእግዚአብሔር በመታመናቸው በሚያቃጥል የእሳት ነበልባል ውስጥ በመጣል፣ ወደ አንበሳ ጉድጓድ በመወርወር፣ በሰይፍ በመተርተር እምነታቸውን ገልጠዋል፡፡ እግዚአብሔርም በቅዱሳን የእምነት ጥንካሬ የልበ ደንዳኖችን ልብ ማርኳል፡፡ «ንጉሡ ናቡከደነጾር ለጣዖት አንሰግድም ብለው እምነታቸውን የገለጡትን ሠለስቱ ደቂቅን ርዝማኔው አስራ ስድስት ክንድ ከሚደርስ የእሳት ነበልባል ውስጥ በሰንሰለት አስሮ ቢወርወራቸውም ከሰውነታቸው አንዳች ሳይቃጠል በመዳናቸው፤ «በእርሱ የታመኑትን ባሪያዎቹን ያዳነ የሲድራቅ፣ የሚሳቅና የአብ ደናጎ አምላክ ይባረክ» ዳን. 3፣25 ሲል የሠለስቱ ደቂቅን አምላክ አክብሯል፡፡

በዘመነ ሐዲስ በሰው ፍቅር ተስቦ ወደዚህ ዓለም የመጣው ቸሩ አምላክ ለአገልግሎት ከመረጣቸው ሰዎች አንዳንዶቹ ምንም ዓይነት መሠረታዊ የሃይማኖት ዕውቀት አልነበራቸውም፡፡ እግዚአብሔር እነዚህን አላዋቂዎችን የመረጠው በዘመኑ በዕውቀታቸው የሚታበዩ ሰዎችን ዕውቀት ከንቱ ለማድረግ ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ጌታችን የዓለምን ጥበብ ከንቱ ለማድረግ አላዋቂዎችን እንደመረጠ ሲያስረዳ፤ «እግዚአብሔር ጥበበኞችን እንዲያሳፍር የዓለምን ሞኝ ነገር መረጠ፤ ብርቱንም ነገር እንዲያሳፍር እግዚአብሔር የዓለምን ደካማ ነገር መረጠ፤ እግዚአብሔር የሆነውን ነገር እንዲያጠፋ የዓለምን ምናምንቴ ነገር የተናቀውንም ነገር ያልሆነውንም መረጠ፡፡» ብሏል፡፡ 1ኛቆሮ.1፣26-29፡፡

እግዚአብሔር ለእምነት አገልግሎት ሰዎችን ሲመርጥ ሞኞች ጠቢባን ይሆናሉ፤ አላዋቂዎች ሀብተ እውቀት ያገኛሉ፤ ደካማዎች ብርቱዎች ይሆናሉ፡፡ አላዋቂ የነበሩት ተከታዮቹ ጠቢባን፤ ደካማ የነበሩት ብርቱዎች እስከሚሆኑ ድረስ ለቀጣይ የእምነት ሕይ ወታቸው ብርታት እንዲሆናቸው የተለያዩ ጥያቄዎችን ለጌታችን ያቀርቡ ነበር፡፡

ጌታችን እና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ይከተሉ ከነበሩ ሰዎች ለጌታችን ካቀረቡት ጥያቄ አንዱ «አለማመኔን እርዳው» የሚል ነው፡፡ ጌታችን የቃሉን ትምህርት ሰምተው የእጁን ተአምራት አይተው የተከተሉትን በሕይወት ሰጪ ትምህርቱ በነፍስ የተመሙትን ተስፋ የቆረጡትን፣ ባዶነት የሚሰማቸውን መንፈሳዊ ዝለት የገጠማቸውን ሲፈውስ፤ በተአምራቱ ደግሞ በሕማመ ሥጋ የታመሙትን ፈውሷል፡፡ የጌታችንን ሕይወት ሰጪ ትምህርት ፈልገው የተከተሉ አብዛኛዎች በተከፈለ ልብ ነበር፡፡ መድኃኒታችን የተከፈለ ልብ ያላቸውን ማረጋጋት፣ ያዘኑትን ማጽናናት ግብሩ በመሆኑ ድክመታቸውን ሳይሸሸጉ የሚቀርቡትን ፈጣን ምላሽ ይሰጣል፡፡

የጌታችን ደቀ መዛሙርት ልጁን እንዲፈውሱለት የወሰደው ሰው፤ ከእርሱና ከደቀ መዛሙርቱ የእምነት ማነስ የተነሣ ፍቱን መፍትሔ ቢያጣም ከጌታችን ዘንድ መጥቶ የእምነቱ ጉድለት በጌታችን እንዲስተ ካክልለት የልጁን ሕማም ሁኔታ ከዘረዘረ በኋላ፤ «ቢቻልህ ግን እዘንልን እርዳን» ማር.9፣22 የሚል ጥያቄ አቅርቧል፡፡ ሁሉን ቻይ የሆነው አምላክ «ቢቻልህ የሚለውን» የጥርጣሬ ቃል «ቢቻልህ ትላለህ፤ ለሚያምን ሰው ሁሉ ይቻላል፡፡» በሚል ቃል ሲያርመው የተቸገረው ሰው አለማመኑ በእርሱ እንዲጠገንለት «በታላቅ ድምፅ አምናለሁ፤ አለማመኔን እርዳው» ብሎታል፡፡ ይህ ሰው አምናለሁ አለማመኔን እርዳው በማለት በእምነት ሕይወት ውስጥ ያለበትን ችግር ሳይሸሸግ መናገሩን ማስተዋል ያስፈልጋል፡፡

ምክንያቱም እያመን የማናምን፣ ንስሐ እየገባን የማንፀፀት፣ እየቆረብን ለሥጋ ወደሙ ክብር የማንሰጥ፣ እየቀደስን ያልተቀደስን ብዙዎች ነን፡፡ እኛም እናምናለን ነገር ግን እምነታችን በአንተ ይታገዝ እርዳን ብለን መጠየቅ አለብን፡፡ ብዙ ሰዎች ክርስቶስ መወለዱን፣ መጠመቁን፣ ከሙታን መነሣቱን (ትንሣኤውን መግለጡን) ያምናሉ፡፡ በዚህ ሕይወት ውስጥ ያላቸውን ድርሻ እና ተስፋ ግን ይጠራጠራሉ፡፡ በሌላ አነጋገር እያመንን በእምነት ሕይወት ውስጥ አንኖርም ለዚህ ማለዘቢያ ግን እምነታችን፣ አለማወቃችንና ድካማችን በጌታችን እንዲደገፍ መማጸን ነው፡፡

በማቴዎስ ወንጌል ቅዱሳን ሐዋርያት የታመመውን ልጅ ለመፈወስ አቅም ያጡበትን ምክንያት ለመረዳት፤ «እኛ ልናወጣው ያልቻልን ስለምንድነው?» ሲሉ ጌታችንን ጠይቀውታል /ማቴ.17፣19/፡፡ ይህ ጥያቄ የእኛም ጥያቄ ነው፡፡ እኔ የተሰጠኝን ሓላፊነት ያልተወጣሁት ስለምንድነው? ያልቆረብኩት ስለምንድነው? ከልቤ ውስጥ የሚጉላላውን ቂም ያላወጣሁት ስለምንድነው? የበደልኩትን ያልካስኩት ስለምንድነው? የሚፈታተነኝን የሰይጣን ፈተና ማለፍ ያልቻልኩት ስለምንድነው? መንፈሳዊ ሕይወቴ ማደግ ያልቻለው፣ ራሴን ማወቅ መረዳት ያልቻልኩት ስለምንድነው? ብለን እንድንጠይቅ የቅዱሳን ሐዋርያት ጥያቄ ይጋብዘናል፡፡

ቅዱሳን ሐዋርያት እግዚአብሔር ከጎናቸው እያለ የእምነት ጉድለት ስለታየባቸው ማድረግ የሚገባቸውን ለመፈጸም አልቻሉም፤ ነገር ግን ልባቸውን የፈነቀለውን አንገብጋቢ ጥያቄ መጠየቃቸው መልካም ነበር፡፡ ምክንያቱም በእምነት ሊያደርጉት የሚቻላቸውን ነገር ማድረግ የተሣናቸው ስለእምነታቸው ጉድለት መሆኑን ጌታችን አስረግጦ እንዲህ በማለት ነግሯቸዋል፡፡ «እውነት እላችኋለሁ የሰናፍጭ ቅንጣት የሚያህል እምነት ቢኖራችሁ ይህን ሾላ ተነቅለህ በሌላ ቦታ ተተከል ብትሉት ይታዘዝላች ኋል» ሉቃ.17፣6 ብሏቸዋል፡፡ «ማመን፣ ያመኑትን ማድረግ» ከባድ ነገር ነው፡፡ ዛሬ ስለእምነት፣  በእምነት ሕይወት ስለመኖር፣ የእግዚአብሔርን ቃል መሠረት በማድረግ የቅዱሳንን ገድልና ትሩፋት በመግለጥ ብዙ ነገር ተነግሮናል፡፡ ነገር ግን በአብዛኛዎቻችን ቃሉ በጭንጫ ላይ የተዘራ ዘር ሆኖብናል፤ /ማቴ. 13፣20/ «ጌታችን በጭንጫ ላይ ዘር ወደቀ፤ ጥልቅ መሬትም ስላልነበረው ወዲያው በቀለ፤ ፀሐይ በወጣ ጊዜ ግን ደረቀ» ያለውን ሲፈታ «በጭንጫ ላይ የተዘራውም ይህ ቃሉን ሰምቶ ወዲያው በደስታ የሚቀበል ነው፡፡ ነገር ግን ለጊዜው ነው እንጂ በእርሱ ሥር የለውም፤ በቃሉ ምክንያት መከራ ወይም ስደት በሆነ ጊዜ ወዲያው ይሰናከላል፡፡» ብሏል፡፡

በእምነት መንፈሳዊ ሕይወታቸው አልጸና ብሎአቸው ይቸገሩ የነበሩ ቅዱሳን አባቶቻችን ያቀረቡት ጥያቄ መሠረታዊ ምላሽ አግኝቶ፤ የሰውነ ታቸው ለልብሳቸው፤ የልብሳቸው ለጥላቸው አልፎ ሕሙም ከመፈወስ ሙት እስከ ማስነሣት ደርሰዋል፡፡ ይኸውም ጥያቄያቸው ተቀባይነት አግኝቶ በዚህም አገልግሎታቸው እንደ ሠመረላቸው መረዳት ይቻላል፡፡

እኛም «በሃይማኖት ስትኖሩ ራሳች ሁን መርምሩ» ተብሎ እንደተነገረን፤ በቅድሚያ መንፈሳዊ ሕይወቴ ያላደገው ለምንድ ነው? ብለን ያለንን የእምነት ጥንካሬና ድክመት መመዘን አለብን፡፡ በማስከተል እንደ ታመመው ልጅ አባት «አለማመኔን እርዳው» የሚል ጥያቄ አቅርበን፤ የሰናፍጭ ቅንጣት የምታህል ፍጹም እምነት ሲኖረን ጌታችን እንዳለው ተራራ የሆነብን ትዕቢት፣ ከፊታችን የተደ ቀነው ክፋት፣ ምቀኝነት ከሕይወ ታችን ይነቀላል፡፡ እየወላወለ የሚያ ስቸግረን ልቡናችን ክት እንዲሆን ወይም እንዲሰበሰብልን «አለማመኔን እርዳው» ማለት አለብን፡፡ አለማመናችን በእግዚአብሔር ሲረዳ ባሕሩ እንደ የብስ ጸንቶልን እንደ ቅዱስ ጴጥሮስ በባሕር ላይ እንረማመዳለን፡፡ በሌላ አነጋገር እግዚአብሔር አለማመናችንን ሲረዳው የሚሣነን ነገር የለም፡፡ «በእኔ የሚያምን ከእኔ የበለጠ ያደርጋል» ተብሎ ለቅዱሳን የተገባው ቃል የታመነ ነው፡፡ 

ያ በእምነት ያልጸናው ሰው ለእግዚአብሔር አምላኩ «አለማመ ኔን እርዳው» ሲል ያቀረበው ጥያቄ የሁላችንንም ሕይወት የሚወክል ነው፡፡ ዛሬ እምነቱ ሥርዓቱ፣ ትውፊቱ እያ ለን በፍጹም ልብ ያለማመን ችግር አለብን፡፡ ልጁ የታመመበት ሰው «አለማመኔን እርዳው ሲል» በአንተ ታምኜ የምኖርበትን ኃይል ለአንተ የሚገዛ ልብ እና ሕይወት ስጠኝ ማለቱ እንደሆነ መረዳት ያስፈልጋል፡፡

ከአባቶቻችን የተቀበልነው እምነት የፈተና ጎርፍ ሳይሸረሽረው ነፋስ ሳያ ዘመው በዐለት ላይ ተመሥርቶ እን ዲጸናልን ዘወትር «ጌታ ሆይ አለማ መኔን እርዳው» ማለት አለብን፡፡ ያለማመናችን ችግር በእግዚአብሔር ካልተረዳ «ጌታ ሆይ ጌታ ሆይ» በማለት ብቻ መንግሥተ ሰማያትን እንደማንወርስ ተነግሮናል፡፡ በመሆ ኑም ልባሞች ከመብራታቸው ጋር ዘይት ይዘው ሙሽራውን እንደጠበቁ፤ ባለማመን የጠወለገውን ሕይወታ ችንን በቃሉ ዝናምነት በማለምለም አለማመናችን በእግዚአብሔር ቃል መረዳት አለበት፡፡

ማንኛውም የሕይወት ውጣ ውረድ ቢያጋጥመን በእምነት ከጸናን የማናልፈው ነገር የለም፡፡ የማንዘለው የችግር እና የመከራ ግንብ፣ የማንሻገረው ባሕር እና መሰናክል የለም፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት በእምነት ከእግዚአብሔር ጋር ከኖርን የሚያስፈራን አንዳች ነገር አለመኖሩን ሲያስረዳ «በሞት ጥላ መካከል እንኳን ብሔድ፤ አንተ ከእኔ ጋር ነህና ክፉን አልፈራም፤ በትርህና ምርኩዝህ እነርሱ ያጽናኑኛል» መዝ. 22፣4 ብሏል፡፡

ነቢዩ እንደ ነገረን አፋችንን ሞልተን «በሞት ጥላ መካከል እንኳን ብሔድ ክፉን አልፈራም» በማለት በእምነት ማደግ አለብን፡፡ ቅዱስ ዳዊት በሕይወት ዘመኑ መውደቅ መነሣት ያጋጠመው ሰው ቢሆንም በእምነት በመጽናቱ ፍጻሜው ሠምሮ ልበ አምላክ ለመባል በቅቷል፡፡ በመሆኑም ዛሬ በመንፈሳዊ ሕይወታችን የተደቀነብንን ፈተና የምናልፈው በእምነት ነው፡፡ እግዚአብሔርን ደስ የምናሰኘው በእምነት ነው፡፡ የሚመጣውን ነገር በተስፋ የሚያስረዳንም እምነት በመ ሆኑ አለማመናችንን እርዳው እያልን መጮህ ይገባል፡፡

አለማመናችን በእግዚአብሔር ሲረዳ ወይም በእምነት ስንጸና ረድኤተ እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ይሆናል፡፡ እግዚአብሔር ኃያላን የሆኑትን አራዊት ሳይቀር ገራም ያደርግልናል፡፡ በዘመነ ብሉይ ነቢዩ ዳንኤል ከአናብስት ጉድጓድ ሲወረወር የተራቡት አንበሶች ለነቢዩ ገራም የሆኑት የእምነት ሰው በመሆኑ ነው፡፡ በቅድስናቸው የተመሰከረላቸው ጻድቁ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ አናምርት /ነብሮች/ እና አናብስት /አንበሶች/ የእግራቸውን ትቢያ እየላሱ የታዘዙላቸው በሥጋዊ ጥበብ ሳይሆን በእምነት ነው፡፡ ዛሬ ዲያብሎስ «እንደተራበ አንበሳ በፊታችን በሚያደባበት ዘመን የእምነትን ጥሩር መልበስ ያስፈልጋል፡፡ ለቀደሙት አባቶች ሥጋት የነበሩት ነገሮች ቀሊልና ታዛዥ እንደሆኑ ለእኛም ይሆኑልናል፡፡ ብዙ ጊዜ ፈቃደ ሥጋችን ፈቃደ ነፍሳችንን ሲጫነው የምንወደውን ሳይሆን የማንወደውን እናደርጋለን፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ «የማልወደውን ክፉን ነገር አደርጋለሁና ዳሩ ግን የምወደውን በጎውን ነገር አላደርገውም» ሮሜ. 7፣19፡፡ ሲል እንደተናገረው፤ የሥጋችን ፈቃድ ብዙ ጊዜ «ነፍሴ ብይ፣ ጠጪ ደስ ይበልሽ» ወደ ማለት ቢያዘነብልም ቅሉ ወደ ፈቃደ ነፍስም መለስ ብሎ እኔ ማነኝ? ጉዞዬስ ወዴት ነው? ተስፋዬስ ማን ነው? ብሎ መጠየቅ ብልህነት ነው፡፡ ቅዱስ ዳዊት ፈቃደ ሥጋው እያየለ ሲያስቸግረው፤ በእንባው መኝታውን እያራሰ በእግዚአብሔር ፊት ቢያለቅስ፤ የኃጢአት አሽክላ እየተ ቆረጠለት በእምነቱ የሚደሰት ሰው ሆኗል፡፡

በእምነት ጉድለት በዲያብሎስ ሽንገላ የእምነት አቅም አጥተን ከቤተ ክርስቲያን ከቅድስና ሕይወት የራቅን ወገኖች፤ አለማመናችንን እግዚአብሔር እንዲረዳው ሳንሰለች ጥያቄ ማቅረብ አለብን፡፡ አስቀድመን እንደገለጽነው በእምነት ጉድለት ምክንያት ያጣነውን በረከት፣ ያጣነውን ጽናት እናገኛለን፡፡ ልባሞቹ ቅዱሳን ሐዋርያት ይህን ለመፈጸም ለምን እኛን ተሳነን? ብለው እንደጠየቁ፤ እኛም ራሳችንን መጠየቅ አለብን፡፡ በጎ መሥራት ለምን ተሳነን?

የሰው ልጅ ወደ እምነት ፍጹም ነት ውስጥ ሲገባ ሁሉ ነገር በእግዚአብሔር እጅ እንደሆነ ይረዳል፤ ከጭንቀትም ያርፋል፡፡

በአቅማችንና በፈቃዳችን የተቸገረን መርዳት፣ አምላክን ከልብ መውደድ፣ ማመስገን የእምነት ሰው መገለጫ ናቸው፡፡

በእምነት የጸኑ አባቶችን በአንበሳ ጉድጓድ፣ በእሳት ውስጥ፣ በወህኒ ቤት በተጣሉ ጊዜ የተረዳና የእምነታቸውን ዋጋ የከፈለ እግዚአብሔር ዛሬም አለ፡፡ በመሆኑም መንፈሳዊ ሕይወታችንን በእምነት አሳድገን ተስፋ መንግሥተ ሰማያትን ለመውረስ ያብቃን፡፡

  

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

Zimare_Mewasit.JPG

የዝማሬ መዋሥዕት አድራሾች ተመረቁ

በደረጀ ትዕዛዙ
 
Zimare_Mewasit.JPG
 
በዙር አባ አቡነ አረጋዊ ገዳም የዝማሬ መዋሥዕት ትምህርታቸውን ተከታትለው ተመረቁት ደቀ መዛሙርት ከአቡነ እንድርያስ ጋር

በደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት በላይ ጋይንት ወረዳ ሳሊ በተባለው ቀበሌ የሚገኘው የጽርሐ አርያም ዙር አባ አቡነ አረጋዊ ገዳም ዝማሬ መዋሥዕት ትምህርት ቤት ዐሥራ ሰባት የዝማሬ መዋሥዕት አድራሾችን አስመረቀ፡፡

የአብነት ትምህርት ቤቱ ጥር 30 ቀን 2002 ዓ.ም አድራሾችን ባስመረቀበት ወቅት ብፁዕ አቡነ እንድ ርያስ የሀገረ ስብከቱ ሊቀጳጳስ ለተመራቂዎች ባስተላለፉት መልእክት፤ «በብዙ ጥረት እና ድካም፤ በረጅም ጊዜ ያካበታችሁትን ዕውቀት በተለያዩ ጊዜያትና ቦታዎች ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንድታውሉት አደራ እላለሁ» ብለዋል፡፡

ምሩቃኑ ተግተው ቤተክርስቲያንን በማገልገል ሌሎችንም ተተኪ ደቀመዛሙርት ማፍራት እንዳለባቸው ያሳሰቡት ብፁዕነታቸው፤ ሀገረ ስብከታቸው ለዚህ ቅዱስ ተግባር ስኬታማነት የበኩሉን የሓላፊነት ድርሻ ለመወጣት ዝግጁ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡

በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ ላይ የተመራቂ ቤተሰቦች፣ ካህናት፣ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች የተገኙ ሲሆን፤ ዝማሬ፣ ቅኔ መወድስ የአማርኛ እና የግእዝ ቅኔ ግጥሞች በተመራቂዎች መቅረቡን ከደብረ ታቦር ማእከል የደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡ «አድራሽ» ማለት በቤተ ክርስቲያን የአብነት ት/ቤቶች ለመምህርነት የሚያበቃቸውን ሙያ ተምረው ያጠናቀቁ ደቀመዛሙርት ማለት ነው፡፡

Semera_Kidus_Yohanes_Church.jpg

በአፋር ሰመራ ከተማ የመጥምቁ ዮሐንስ ገዳም ቅዳሴ ቤት ተከበረ

ሎጊያ ወረዳ ማዕከል
    Semera_Kidus_Yohanes_Church.jpg
 
 
 
 
 
 
 
በሰመራ ከተማ የተሰራዉ የቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን

በአፋር ሀገረ ስብከት ሰመራ ከተማ በሀገረ ስብከቱና በአካባቢው ማኅበረሰብ ከፍተኛ ጥረት የተሠራው የቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ገዳም መቃኞ ተጠናቆ ቅዳሴ ቤቱ ተከበረ፡፡

ባለፈው ዓመት ሰኔ ወር ላይ ግንባታው የተጀመረው ይኸው መቃኞ ቤተ ክርስቲያን፤ ቤተልሔም፣ የግብር ቤት፣ የዕቃ ቤት እና የውኃ ማጠራቀሚያ ገንዳ እንዲሁም የካህናት ማረፊያ ቤቶችም ጭምር እንደተሠሩለት ታውቋል፡፡

ጥር 30 ቀን 2002 ዓ.ም በርካታ የአካባቢው ምእመናን፤ የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች፣ ካህናትና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት ቅዳሴ ቤቱ ሲከበር ከቀረበው መግለጫ ለመረዳት እንደተቻለው፤ 2001 ዓ.ም በሰመራ ከተማ የተቋቋመው ዩኒቨርስቲ ተማሪዎችን ሲቀበል የክርስቲያኖች ቁጥር ጨምሯል፡፡ ይሁንና በከተማው በወቅቱ ምንም ዓይነት ቤተ ክርስቲያን ባለመኖሩ ማስቀደስ፣ ቃለ እግዚአብሔርን መስማት እንዲሁም ሌሎች የቤተ ክርስቲያን አገልግሎቶችን ማግኘት አልተቻለም ነበር፡፡

በዕለቱ ቡራኬ የሰጡት የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ዮናስ እንደገለጹት፤ ከ1987 ዓ.ም ጀምሮ የአምልኮ ቦታ ለማግኘት ከፍተኛ ጥረት ሲያደርጉ ቆይተው በአፋር ክልላዊ መንግሥት መልካም ፈቃድ 29 ሺሕ 830 ካሬ ሜትር ቦታ ተሰጥቷቸዋል፡፡ ቦታው የመንበረ ጵጵስና፣ የሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት እና የሕንፃ ቤተ ክርስቲያን መሥሪያን ያካተተ ማስተር ፕላን /የይዞታ ማረጋገጫ/ የተሠራለት መሆኑንም ተናግረዋል፡፡

«ይህ ቦታ በረሃማ ስለሆነ፤ በበረሃ የገደመው ዘ ንብረቱ ገዳም በተባለለት በቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ስም፤ ቅሩበ ሳሌም ዮሐንስ መጥምቅ ገዳም ተብሎ እንዲጠራ ይሁን» ያሉት ብፁዕነታቸው፤ ቅሩበ ሳሌም የሚለው ሥያሜ ዮሐንስ መጥምቅ የንስሐ ጥምቀት ያጠምቅበት የነበረው አካባቢ እንዲታወስ መሆኑንም አስረድተዋል፡፡

የገዳሙ ሕንፃ ቤተክርስቲያን /መቃኞ/ መሠራት እጅግ ያስደሰታቸው መሆኑን የገለጹት ብፁዕነታቸው ለሥራው የተባበሩትን ሁሉ በማመስገን ምእመናኑን እንኳን ደስ ያላችሁ ብለዋል፡፡

ከሁለት ዓመት  በኋላ  ዋናውን ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ለማሠራት ዕቅድ መኖሩንም ተናግረዋል፡፡

በሰመራ ከተማ ምንም ዓይነት ቤተ ክርስቲያን ባለመኖሩ የዩኒቨርስቲው ተማሪዎች የእምነት ሥርዓታቸውን ማከናወን ይቸገሩ እንደ ነበር የጠቀሰው የግቢ ጉባኤው ሰብሳቢ ዲ/ን ደጀን፤ ያም ሆኖ ተማሪው ከዩኒቨርስቲው መደበኛ ትምህርት ጎን ለጎን መንፈሳዊ ትምህርት የመቀበል ፍላጎቱ ከፍተኛ ስለነበረ ግቢ ጉባኤ ተቋቁሞ ትምህርቱ ይሰጥ እንደነበር አስረድቷል፡፡

«ቦታው ምድረ በዳ ከመሆኑ አንፃር በእግዚአብሔር ኃይል እንጂ በሰው እጅ ተሠራ ለማለት አያስደፍርም» ያለው ሥራውን በሓላፊነት ሲከታተል የነበረው ዲ/ን ናሁሠናይ ደስታ በበኩሉ፤ «የሕንፃ ቤተ ክርስቲያኑ ሥራ ከጀምሩ አንሥቶ እስኪጠናቀቅ ድረስ ድጋፍ ያደረጉ የሰመራ ዩኒቨርስቲ መምህራንና ሠራተኞች፣ የዱብቲ ውኃ ሥራዎች ድርጅት ሠራተኞች፣ የእመቤታችን ጽዋ ማኅበር፣ የግቢ ጉባኤ ተማሪዎችና የአካባቢው ምእመናን ምስጋና ይገባቸዋል» ብሏል፡፡

በዚህ ሥነ ሥርዓት ላይ የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ዮናስ ከተለያዩ ምእመናን ያገኙዋቸውን ንዋያተ ቅድሳት ለቤተ ክርስቲያኑ መገልገያ ማስረከባቸውንም ከማኅበረ ቅዱሳን የሎግያ ወረዳ ማእከል የተላከልን ዘገባ ያስረዳል፡፡

ሰንበት ትምህርት ቤቶቹ የልምድ ልውውጥ አደረጉ

በይብረሁ ይጥና

ከሲዳማ ሀገረ ስብከት ሀዋሳ ከተማና አካባቢዋ የተውጣጡ የስድስት ሰንበት ትምህርት ቤቶች ተወካዮች በአዲስ አበባ የአምስት ሰንበት ትምህርት ቤቶችን እንቅስቃሴ በመጎብኘት የልምድ ልውውጥ አደረጉ፡፡

ሃያ ዘጠኝ አባላትን ያቀፈው የልኡካን ቡድን፤ በሰንበት ትምህርት ቤቶች መዋቅር አደረጃጀትና አሠራር፣ መዝሙራት፣ የአባላት ክትትልና አያያዝ፣ ሥነ ምግባርና የልማት ጉዳዮች ላይ ውይይት በማድረግም የጋራ ግንዛቤ አግኝቷል፡፡

የልኡካን ቡድኑ አስተባባሪና የሀዋሳ ደብረ ምሕረት ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ሰንበት ትምህርት ቤት አባል ወጣት ብስራት ጌታቸው ለስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ እንዳስታወቀው፤ «ከየካቲት 19 እስከ 21 ቀን 2002 ዓ.ም ድረስ ከመንበረ መንግሥት ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ዓምደ ሃይማኖት፣ መናገሻ ገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ፣ ደብረ ኃይል ቅዱስ ራጉኤል፣ ጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን ፍኖተ ብርሃን እና ከልደታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያን ተክለ ሳዊሮስ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ጋር የልምድ ልውውጥና ውይይት በማድረግ ሰፊ ትምህርት ቀስመናል፡፡» ብሏል፡፡ እንዲሁም፤ «በተለይ የቤተክርስቲያንን ሥርዓት ለማስጠበቅና የሚታዩ ክፍተቶችን ለመሙላት ሰንበት ትምህርት ቤቶች በኅብረት ሆነው መሥራት ጠቃሚ መሆኑን ተረድተናል» በማለት አመልክቷል፡፡

ከአባላቱ መካከል የሀዋሳ ቅዱስ ሩፋኤል ቤተክርስቲያን ሰንበት ትምህርት ቤት ዋና ጸሐፊ ወጣት ሥላስ አዲስ በሰጠችው አስተያየት፤ «ለሦስት ቀናት ባደረግነው ውይይት ጠቃሚና መሠረታዊ የሆነ ነገር አግኝተናል፡፡ ካገኘነውም ተሞክሮ ከተኛንበት እንድንነቃና ሥራዎቻችንን እንደገና እንድንፈትሽ አድርጎናል» ስትል ተናግራለች፡፡

ሌላው በሀዋሳ ደብረ ሰላም ቅድስት ሥላሴ ቤተክርስቲያን ሰንበት ትምህርት ቤት ምክትል ሰብሳቢ ወጣት ይድነቃቸው ጥላሁንም፤ «በአንድ ቤተክርስቲያን ውስጥ ብዙ የአሠራር ልዩነትና ክፍተቶች መኖራቸውን ተረድቻለሁ፡፡ ከዚህ አንፃር እኛ ብዙ መሥራት እንዳለብን ተገንዝቤያለሁ፡፡ በይበልጥ መዝሙራትን በሚመለከት ችግሮች ስላሉ ከጉብኝታትን ባገኘነው ትምህርት ካለፈው በተሻለ ሁኔታ ትኩረት ሰጥተን እንድንሠራ ያደርገናል፡፡ በጠቅላይ ቤተክህነትም አንድ ወጥ በሆነ አሠራር አፈጻጸሙን ለመከታተል ጥረት ቢደረግ በመላው ሀገሪቱ የሚገኙ ሰንበት ትምህርት ቤቶችን ለመቆጣጠር ይመቻል፡፡» ሲል አስተያየቱን ሰጥቷል፡፡

በአዲስ አበባ የመንበረ መንግሥት ግቢ ገብርኤል ገዳም ዓምደ ሃይማኖት ሰንበት ትምህርት ቤት አባል ደነቀ ማሞ በበኩሉ ውይይቱን አስመልክቶ በሰጠው አስተያየት፤ «ከሀዋሳ ከመጡ ስድስት ሰንበት ትምህርት ቤቶች ጋር የልምድ ልውውጥ መደረጉ በሰንበት ትምህርት ቤቶች መካከል የጋራ ግንዛቤ እንዲኖር ያስችላል፡፡ ስለሆነም ሌሎች ሰንበት ትምህርት ቤቶችም ይህን አርአያ ቢከተሉ ጠቀሜታው የጎላ ነው» ሲል ተናግሯል፡፡

ሰንበት ትምህርት ቤቶች በአንድነት ሆነው መወያየታቸው የቤተ ክርስቲያንን ሥርዓትና ትውፊት ለመጠበቅ ትልቅ ድርሻ እንዳለው ይታመናል፡፡