፫.ጾመ ሐዋርያት እና ጾመ ድኅነት

ሰኔ ፲፬ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

እንደሚታወቀው በዓለ ጰራቅሊጦስን ተከትለው ሁለት ዐበይት አጽዋማት ይጀመራሉ፡፡ እነዚህም ጾመ ሐዋርያት እና ጾመ ድኅነት (ረቡዕና ዓርብ) ሲኾኑ፣ ቍጥራቸውም ከሰባቱ አጽዋማት ውስጥ ነው፡፡ ስለኾነም ኹላችንም ልንጾማቸው እንደሚገባ በቤተ ክርስቲያን ሕግ ታዝዟል፡፡ ይህም ከቀደሙ አባቶቻችን ጀምሮ የመጣ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ሥርዓት እንጂ እንግዳ ሕግ አይደለም፡፡

ቅዱሳት መጻሕፍት እንደሚናገሩት በብሉይ ኪዳን ነቢዩ ሙሴ ከእግዚአብሔር ዘንድ የተቀበለውን ሕገ ኦሪት ለሕዝቡ ከማስተማሩ በፊት ጾሟል /ዘፀ.፴፬፥፳፰/፡፡ ቅዱሳን ነቢያትም የተስፋውን ቃል መፈጸም እየተጠባበቁ እግዚአብሔርን ውረድ፤ ተወለድ እያሉ ይጾሙ፣ ይጸልዩ ነበር፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ጾም የምግባር መሠረት መኾኑን ሊያስተምረን ወንጌልን ከመስበኩ አስቀድሞ ጾሟል /ማቴ.፬፥፩-፲፩/፤ ሐዋርያትም በበዓለ ኀምሳ መንፈስ ቅዱስ ከወረደላቸው በኋላ ሕገ ወንጌልን ለሕዝቡ ከማስተማራቸው አስቀድሞ ጾመዋል፡፡

እኛም እነርሱን ተከትለን፣ በእነርሱ ሥርዓት በመመራት፣ በሐዋርያት ላይ ያደረው የመንፈስ ቅዱስ ጸጋና ሀብት በእኛም ላይ እንዲያድርብን በየዓመቱ ጾመ ሐዋርያትንና ሌሎችንም አጽዋማት መጾም እንደሚገባን በቀኖና ቤተ ክርስቲያን ተወስኗል /ፍት.ነገ. ፲፭፥፭፻፹፮/፡፡

ጾመ ድኅነት ስሙ እንደሚያመለክተው የመዳን ጾም ማለት ሲኾን፣ ይህም በብሉይ ኪዳኑ አጽዋማት በጾመ አስቴር እና በጾመ ዮዲት የተተካ የሐዲስ ኪዳን ጾም ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን በሐማ ምክንያት በእስራኤል ላይ ታውጆ የነበረው ሞት በጾመ አስቴር እንደ ተሻረ ኹሉ፣ በሐዲስ ኪዳንም በዕለተ ረቡዕ በጌታችን ላይ በተፈጸመው ምክር የሰይጣን ሴራ ፈርሷልና በጾመ አስቴር ምትክ ረቡዕን እንጾማለን፡፡

እንደዚሁም በብሉይ ኪዳን በጾመ ዮዲት ምክንያት ሆሎሆርኒስ ድል እንደ ተደረገበት ኹሉ፣ በሐዲስ ኪዳንም መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕለተ ዓርብ በመስቀል ላይ በከፈለው መሥዋዕትነት ዲያብሎስ ድል ተደርጓልና በጾመ ዮዲት ምትክ ዓርብን እንጾማለን፡፡ የእነዚህ የሁለቱ ቀናት (የረቡዕና ዓርብ) ጾም ጾመ ድኅነት ይባላል፡፡

በአጠቃላይ ጾመ ሐዋርያትና ጾመ ድኅነት እንደ ጾመ ነነዌና ዐቢይ ጾም የበዓላትና የአጽዋማት ማውጫ ቀመርን ተከትለው የሚመጡ ከሰባቱ አጽዋማት መካከል የሚመደቡ ጾሞች ናቸው፡፡ የጾመ ሐዋርያት ፋሲካ (መፈጸሚያ) የቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ጳውሎስ በዓለ ዕረፍት (ሐምሌ ፭ ቀን) ሲኾን፣ ጾመ ድኅነት ግን ከበዓለ ኀምሳ በስተቀር ዓመቱን ሙሉ የሚጾም ጾም ነው፡፡

ዕለተ ረቡዕ የጌታ ሞት የተመከረበት፤ ዓርብም አምላካችን የተሰቀለበት ዕለት ነውና በመስቀሉ መሥዋዕትነት ያገኘውን ድኅነት ዘወትር ማሰብ ስለሚገባን ሁልጊዜ እንድንጾማቸው በቅዱስ ሲኖዶስ ሥርዓት ተሠርቶልናል፡፡ በዚህ ዓመት ጾመ ሐዋርያት ሰኔ ፲፫፤ ጾመ ድኅነት ደግሞ ሰኔ ፲፭ ቀን ይጀመራሉ፡፡

በመኾኑም የምንጠቀመው በራሳችን መልካም ተግባር፤ የምንወቀሰውም በራሳችን መጥፎ ድርጊት መኾኑን ተረድተን ይኼ የቄሶች፤ ይኼ የመነኰሳት ነው የሚል ሰበብ ሳንፈጥር ኹላችንም በአንድነት ብንጾማቸው ከእግዚአብሔር ዘንድ የምናገኘው ጸጋና ሀብት ይበዛልናልና ራሳችንን ለጾም እናዘጋጅ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የጰራቅሊጦስ መዝሙርና ምንባባት

ሰኔ ፲፬ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዓለ ጰራቅሊጦስ ከዘጠኙ የጌታችን ዐበይት በዓላት አንዱ ሲኾን በዕለቱ በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን የሚዘመረው የቅዱስ ያሬድ መዝሙርም ይትፌሣሕ የሚለው የትንሣኤ መዝሙር ነው፡፡ እንደ መዝሙሩ ኹሉ በጰራቅሊጦስ በዓል በቅዳሴ ጊዜ የሚነበቡ የቅዱሳት መጻሕፍት ክፍሎችም በትንሣኤ ዕለት የተነበቡት ምንባባት ናቸው፡፡

እነዚህም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ በመነሣቱ፣ በማረጉና መንፈስ ቅዱስን ለሐዋርያት በመላኩ፤ እንደዚሁም ሥጋውን ቈርሶ፣ ደሙን አፍስሶ የሰውን ልጅ ከዘለዓለም ሞት በማዳኑ የሰው ዘር ብቻ ሳይኾን የሰማይ መላእክት፣ የምድር ፍጥረታት ሳይቀሩ ሐሤት እንደሚያደርጉ፤ ምድርም በክርስቶስ ደም በመንጻቷ የጌታችንን ትንሣኤ በደስታ እንደምታከብር ያስረዳሉ፡፡

በበዓለ ጰራቅሊጦስ ውስጥ ባሉት ሰንበታት (እሑዶች) የሚዘመሩ መዝሙራት ትንሣኤን፣ ዕርገትንና የመንፈስ ቅዱስን መውረድ የሚያስረዱ ሲኾኑ፣ ዓላማቸውም ከሙታን ተለይቶ ለተነሣው፣ አዳምና ልጆቹን ከዲያብሎስ ባርነትና ከሲኦል ላወጣቸው ለልዑል እግዚአብሔር ምስጋና ማቅረብ ነው፡፡

እንደ መዝሙሩ ኹሉ በጰራቅሊጦስ በዓል በቅዳሴ ጊዜ የሚነበቡ የቅዱሳት መጻሕፍት ክፍሎችም በትንሣኤ ዕለት የተነበቡ ምንባባት ሲኾኑ፣ እነዚህም የሚከተሉት ናቸው፤

ከጳውሎስ መልእክታት፡- ፩ኛ ቆሮንቶስ ፲፭፥፳-፵፩፤

ከሌሎች መልእክታት፡- ፩ኛ ጴጥሮስ ፩፥፩-፲፫፤

የሐዋርያት ሥራ ፪፥፳፪-፴፯፤

ምስባክ፡- መዝሙር ፻፲፯፥፳፬፤

ወንጌል፡- ዮሐንስ ፳፥፩-፲፱፤

ቅዳሴ፡- ዲዮስቆሮስ፡፡

በዓለ ጰራቅሊጦስ፣ ጾመ ሐዋርያትና ጾመ ድኅነት

ሰኔ ፲፬ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

የተወደዳችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች ሰኔ ፲፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በዓለ ጰራቅሊጦስ በሚል ርእስ አቅርበነው የነበረውን ጽሑፍ ለንባብ እንዲያመች በዓለ ጰራቅሊጦስ፣ የጰራቅሊጦስ መዝሙርና ምንባባት፣ እንደዚሁም ጾመ ሐዋርያትና ጾመ ድኅነት በሚሉ ሦስት ንዑሳን አርእስት ከፋፍለን እንደሚከተለው አቅርበነዋል፤

፩.በዓለ ጰራቅሊጦስ

*ጰራቅሊጦስ* የሚለው ቃል ከሦስቱ አካላት አንዱ ለኾነው ለእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ መጠሪያ ስሙ ሲኾን፣ ትርጕሙም በጽርዕ (ግሪክ) ቋንቋ ናዛዚ (የሚናዝዝ)፣ መጽንዒ (የሚያጸና)፣ መስተፍሥሒ (የሚያስደስት) ማለት ነው፡፡ በዓለ ጰራቅሊጦስ በሌላ ቃል በዓለ ጰንጠቆስጤ በመባልም ይታወቃል፡፡ ይኸውም በግሪክ ቋንቋ በዓለ ኀምሳ፣ የፋሲካ ኀምሳኛ ዕለት፣ በዓለ ሠዊት (የእሸት፣ የመከር በዓል) ማለት ነው /ኪዳነ ወልድ ክፍሌ፣ ገጽ ፱፻፮ እና ፱፻፯/፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ካረገ በኋላ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፣ ፲፪ቱ ደቀ መዛሙርት፣ ፸፪ቱ አርድእት፣ ፭፻ው ባልንጀሮችና ፴፮ቱ ቅዱሳት አንስት በኢሩሳሌም ከተማ በአንድነት ኾነው ለጸሎት ይተጉ ነበር፡፡ በሚያርግበት ጊዜም *እነሆ አባቴ የሰጠውን ተስፋ እኔ እልክላችኋለሁ፤ እናንተ ግን ከላይ ኃይል እስክትለብሱ ድረስ በኢየሩሳሌም ከተማ ቆዩ፤* /ሉቃ. ፳፬፥፵፱/ ሲል ለሐዋርያቱ በገባላቸው ቃል መሠረት ባረገ በ፲ኛው ቀን መንፈስ ቅዱስን ልኮላቸዋል፡፡

በሐዋርያት ሥራ እንደ ተጻፈው በበዓለ ጰራቅሊጦስ ማለዳ ኹሉም በአንድ ቦታ ተሰብስበው ሳሉ እንደ ዐውሎ ነፋስ ያለ ድምፅ ድንገት ከሰማይ መጣና የነበሩበትን ቤት ሞላው፡፡ ከዚያም እንደ እሳት የተከፋፈሉ የእሳት ላንቃዎች በኹሉም ላይ ተቀመጡባቸው፡፡ በዚህ ጊዜ ኹላቸውም መንፈስ ቅዱስን ከተሞሉ በኋላ መንፈስ ቅዱስ ባደላቸው መጠን በየአገሩ ቋንቋዎች ኹሉ መናገር ጀመሩ /ሐዋ.፪፥፩-፬/፡፡ ጌታችን መንፈስ ቅዱስን ለሐዋርያት የላከበት ይህ ዐቢይ በዓል ጰራቅሊጦስ ይባላል፡፡

ጌታችን ከሙታን ተለይቶ ከተነሣ ከ፶ኛው፤ ከዐረገ ከ፲ኛው ቀን ጀምሮ እስከሚቀጥለው እሑድ ድረስ ያለው ወቅትም ዘመነ ጰራቅሊጦስ ተብሎ የሚጠራ ሲኾን፣ ይህ በዓል ካህናተ ኦሪት ዐሥራቱን፣ በኵራቱን፣ ቀዳምያቱን ይቀበሉበት ነበርና በብሉይ ኪዳን በዓለ ሠዊት ይባል ነበር፡፡ በበዓለ ጰራቅሊጦስም ቅዱሳን ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስን ተቀብለውበታልና በበዓለ ሠዊት ምትክ በዓለ ጰራቅሊጦስ ገብቶበታል፡፡

የበዓለ ትንሣኤ መነሻው የአይሁድ የፋሲካ በዓል ማለትም በግብፅ እስራኤል ከሞት የዳኑበት የመታሰቢያ በዓል እንደ ኾነው ኹሉ፣ ለበዓለ ጰራቅሊጦስም መነሻው ይኸው የአይሁድ የፋሲካ በዓል ነው፡፡ የአይሁድ ፋሲካ ከተከበረ ከሰባት ሳምንታት በኋላ በ፶ኛው ቀን የሩቆቹ ከከተሙበት ወጥተው፣ የቅርቦቹ ከተሰባሰቡበት ተገናኝተው ለበዓሉ ፍጻሜ የሚኾነውን በዓለ ሠዊት ያከብሩ ነበር፡፡

ከግብፅ እስከ ከነዓን ምድር የደረሰው የእንስሳት መሥዋዕት ሲጠናቀቅ በ፶ኛው ቀን ይሰባሰብ የነበረው የአይሁድ ጉባኤም መንፈስ ቅዱስ ከወረደበት ዕለት ጀምሮ ተበትኗል፡፡ መሥዋዕተ ኦሪቱ በአማናዊው መሥዋዕት በኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋና ደም እንደ ተለወጠ ኹሉ ጉባኤ አይሁድም በኢየሩሳሌም ከተማ በተሰበሰቡ በቅዱሳን ሐዋርያት ጉባኤ ተለውጧል (ተቀይሯል)፡፡ ይህችውም ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ *ከኹሉ በላይ በምትኾን፣ ሐዋርያት በሰበሰቧት በአንዲት፣ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን እናምናለን፤* እንዳሉ ሠለስቱ ምእት /ጸሎተ ሃይማኖት/፡፡

ሐዋርያት በጽርሐ ጽዮን ተሰብስበው ሳሉ መንፈስ ቅዱስ በእሳት አምሳል ወርዶ ሰማያዊ ሀብትን፣ ዕውቀትና ጸጋን አድሏቸዋል፡፡ መንፈስ ቅዱስ ከወረደላቸው በኋላም በአእምሮ ጎልምሰዋል፤ ጥቡዓን (ቈራጦች)፣ ጽኑዓን ኾነዋል፤ ለስብከተ ወንጌል የሚፋጠኑበትንና ለሰማዕትነት የሚዘጋጁበትን ልቡና ታድለዋል፡፡ ቀድሞ ይናገሩት ከነበሩት ከዕብራይስጥ ቋንቋ በተጨማሪ ፸፩ ቋንቋዎች ተገልጸውላቸው ምሥጢራትን መተርጐም ጀምረዋል፡፡ ሐዋርያት በየገአሩ ቋንቋ ሲናገሩ የሰሙ ከአይሁድ ወገን አንዳንዶቹም ሐዋርያትን *ጉሽ ጠጅ ጠጥተው ሰክረው የኾነ ያልኾነውን ይቀባጥራሉ* ይሏቸው ነበር፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስም ይህንን ዐሳባቸውን በመንፈስ ቅዱስ አውቆ *ሰክረዋል የምትሉ እናንተ እንደምትጠራጠሩት አይደለም፡፡ ጊዜው ማለዳ፣ ሰዓቱም ገና ሦስት ሰዓት ነውና፡፡ ዳሩ ግን በነቢዩ ኢዩኤል ከዚህም በኋላ እንዲህ ይሆናል፤ መንፈሴን በሥጋ ለባሽ ሁሉ ላይ አፈስሳለሁ፤ ወንዶችና ሴቶች ልጆቻችሁም ትንቢት ይናገራሉ፤ /ኢዩ.፪፥፳፰/ ተብሎ የተነገረው ትንቢት ይፈጸም ዘንድ ይህንን ድንቅ ተአምር ያደረገው እናንተ የሰቀላችሁት ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፤* በማለት ሐዋርያት ኢየሱስ ክርስቶስ ነቢያት ትንቢት የተናገሩለት፣ ምሳሌ የመሰሉለት አምላክ ወልደ አምላክ መኾኑን፣ ከሙታን ተለይቶ መነሣቱን፣ ማረጉንና ዳግም በክብር በምስጋና መጥቶ በሕያዋንና በሙታን ላይ የሚፈረድ መኾኑን እንደሚመሰክሩ በአይሁድ ፊት አሰምቶ ተናገረ፡፡

በቅዱስ ጴጥሮስ ትምህርት የተማረኩ አሕዛብም *ምን እናድርግ* ብለው በጠየቁት ጊዜ ከክፋታቸው ተመልሰው፣ ንስሐ ገብተው በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እንዲጠመቁ ነገራቸው፡፡ በዚያችም ሰዓት ሦስት ሺህ ሕዝብ በኢየሱስ ክርስቶስ አምኖ ተጠምቋል /ሐዋ.፪፥፩-፵፩/፡፡ ይህም ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስ ከወረደላቸው በኋላ ያደረባቸው የማሳመን ጸጋና ተአምራትን የማድረግ ኃይላቸው እንደ በዛላቸው ያመላክታል፡፡

ይህ ዕለት ሀብተ መንፈስ ቅዱስ የተሰጠበትና ብዙ ሺሕ ምእመናን የተገኙበት ዕለት በመኾኑ ሊቃውንት የቤተ ክርስቲያን የልደት ቀን በማለት ይጠሩታል፡፡

ቅዱሳን ሐዋርያት *በዚህች ቀን በሦስት ሰዓት ኢየሱስ ክርስቶስ ጰራቅሊጦስን ልኮልናልና በላያችን ኃይልን ሞላ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ በሕያዋንና በሙታን ይፈርድ ዘንድ ሥልጣን እንዳለው በአዲስ ቋንቋ ተናገርን፤* በማለት በዕለቱ ያዩትንና የተደረገላቸውን፣ እንደዚሁም ስለ በዓሉ ታላቅነት ከመሰከሩ በኋላ ይህንን በዓል ማክበር እንደሚገባ አዝዘዋል፤ በአንጻሩ በዚህ ወቅት (በበዓለ ኀምሳ) መጾምና ማዘን ተገቢ አለመኾኑንም ተናግረዋል /ዲድስቅልያ ፴፥፴፰-፴፱፤ ፴፩፥፷፱-፸/፡፡

በአባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ስም የተገነባው ዘመናዊ ሕንጻ ተመረቀ፡፡

ሰኔ ፲፫ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በደመላሽ ኃይለ ማርያም

በደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት በከላላ ወረዳ ቤተ ክህነት በ፳፻፫ ዓ.ም በሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ በብፁዕ አቡነ አትናቴዎስ መሠረቱ የተቀመጠው፣ ከስምንት ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተደረገበት በአባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ስም የተገነባው ባለ ሦስት ፎቅ ኹለገብ ዘመናዊ ሕንጻ ሰኔ ፲፪ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ተመረቀ፡፡

በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ ላይም ብፁዕ አቡነ አትናቴዎስ የደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል፤ ብፁዕ አቡነ እንድርያስ የሊቃውንት ጉባኤ ሓላፊ፣ የመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል የበላይ ጠባቂና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል፤ የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጸሐፊ አቶ ተስፋዬ ቢኾነኝና ሌሎችም የማኅበሩ ሥራ አመራርና ሥራ አስፈጻሚ አባላት፣ የዞኑ የመንግሥት ባለ ሥልጣናት፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና በርካታ ምእመናን ተገኝተዋል፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጸሐፊ አቶ ተስፋዬ ቢኾነኝ የመክፈቻ ንግግር ባደረጉበት ወቅት ማኅበሩ ከሚሠራቸው ፻፳ወ፮ (126) ፕሮጀክቶች መካከል ይህ የአባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ፕሮጀክት አንዱ መኾኑን ገልጸው፣ ከመሠረቱ መቀመጥ ጀምሮ እስከ ፍጻሜው ድረስ የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስና የየመምሪያ ሓላፊዎች ላደረጉት አስተዋጽኦ ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

ይህ ዘመናዊ ሕንጻ በከተማው ካሉት አራት ሕንጻዎች መካከል አንዱ ሲኾን፣ በውስጡም ለእንግዳ ማረፊያ አገልግሎት የሚውሉ ዐሥራ ስምንት ክፍሎች፣ የባንክ ወይም የምግብ አገልግሎት የሚሰጥ ክፍል፣ ለንግድ ሥራ የሚኾኑ ሱቆች እና ሌላም ሥራ ሊሠራባቸው የሚችሉ ክፍሎችን የያዘ ሲኾን፣ ከዚህ ኹሉ አገልግሎት የሚገኘው ገንዘብ ተሰብስቦ ለደብረ ባሕርይ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ እና አባ በጸሎተ ሚካኤል ገዳም አገልግሎት ማጠናከሪያነት እንደሚውል የቅዱሳት መካናት ልማት እና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ዳይሬክተር የኾኑት ዲ/ን አእምሮ ይሄይስ አስረድተዋል፡፡

ዲ/ን አእምሮ አያይዘውም የአባ ጊዮርስ ዘጋሥጫ ዘመናዊ ሕንጻ በሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ በብፁዕ አቡነ አትናቴዎስ የበላይ ሓላፊነት በሚዋቀረው ኰሚቴ እንደሚመራ ገልጸው፣ በዚህም የማኅበረ ቅዱሳን ድጋፍ የሚቀጥል መኾኑን ተናግረዋል፡፡

በመጨረሻም ብፁዕ አቡነ አትናቴዎስና ሌሎች የክብር እንግዶች ሕንጻውን ከጐበኙ በኋላ በአባቶች ጸሎት እና ቡራኬ የመርሐ ግብሩ ፍጻሜ ኾኗል፡፡

የ፭ኛው አገር ዓቀፍ የሰ/ት/ቤቶች አንድነት ጠቅላላ ጉባኤ አጭር ዳሰሳ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሰኔ ፲፫ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ከ፳፻፬ ዓ.ም ጀምሮ በየዓመቱ በበዓለ ጰራቅሊጦስ ሳምንት የአንድነት ጉባኤውን ያካሒዳል፡፡

በያዝነው ዓመትም ከሰኔ ፲-፲፪ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ለሦስት ቀናት በቆየው ጉባኤ የየአህጉረ ስብከቶች ሰ/ት/ቤቶች ሪፖርቶችና ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበዋል፡፡

ለሦስት ቀናት በቆየው በዚህ የሰንበት ት/ቤቶች ጠቅላላ የአንድነት ጉባኤ ወቅታዊ የቤተ ክርስቲያን ጉዳዮች፣ እንደዚሁም የወጣቶች የአገልግሎት ፈተናዎችና መፍትሔዎቻቸው፣ በ፳፻፰ ዓ.ም የአገልግሎት ዘመን የሰ/ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያና የሰ/ት/ቤት ወጣቶች ጠንካራና ደካማ ጎኖች ተዳስሰዋል፡፡

ሰኔ ፱ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም የአሕዛብንና የተሐድሶ መናፍቃንን እንቅስቃሴ በሚመለከት ብፁዕ አቡነ ሉቃስ በተገኙበት ለጉባኤው የቀረበው ጥናታዊ ጽሑፍ ከፍተኛ መነቃቃትን ፈጥሯል፡፡

በጉባኤው መዝጊያ ዕለትም የ፳፻፱ ዓ.ም ዕቅድ የትኩረት አቅጣጫዎችን አስመልክቶ ሰፊ ውይይት ተካሒዷል፡፡

በውይይቱም የሰንበት ትምህርት ቤት አባላት የዕድሜ ገደብና የሥራ አስፈጻሚዎች የአገልግሎት ዘመን መሻሻል አለበት ተብሏል፡፡

በተጨማሪም የ፳፻፱ ዓ.ም ዓመታዊ የተግባር ዕቅድ በጉባኤው ውይይት ከተደረገበት በኋላ ዕቅዱ ጸድቆ ሥራ ላይ እንዲውል ተወስኗል፡፡

የ፳፻፱ ዓ.ም የመሪ ዕቅዱ ግቦች፡- ቤተ ክርስቲያን የሰ/ት/ቤት አገልግሎትን ለማስፋትና ለማጠናከር መዘገጀቷን ማሳወቅ፣ በዓላማው ዙሪያ ሕዝቡን በስፋት ማነሣሣትና ለተግባር ማንቀሳቀስ፤ ቢጽ ሐሳውያንን የመከላከል ዘመቻ፤ እንደዚሁም የሰ/ት/ቤቶችን ሥርዓተ ትምህርት የማስቀጠልና የመከለስ ጥናት ሲኾኑ፣ በመሪ ዕቅዱ በመጀመሪያ አንድ ዓመት ከመንፈቅም፡- የሰንበት ት/ቤቶችን የዝማሬ ሥርዓት እና የሰንበት ት/ቤቶችን አንድነት መዋቅር ማጠናከር የሚሉ ነጥቦች ተካተዋል፡፡

በጉባኤው መዝጊያ ዕለት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት እና ብፁዕ አቡነ ማትያስ ካልዕ የካናዳ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል የተገኙ ሲኾን፣ በዕለቱ ቅዱስ ፓትርያርኩ ‹‹አንትሙሰ ንበሩ በኢየሩሳሌም እስከ ትለብሱ ኃይለ እምአርያም፤ እናንተ ግን ከላይ ኀይል እስክትለብሱ ድረስ በኢየሩሳሌም ከተማ ቆዩ፤›› /ሉቃ.፳፬፥፵፱/ በሚል ኃይለ ቃል ትምህርተ ወንጌል ሰጥተዋል፡፡

ቅዱስነታቸው ትምህርት በሰጡበት ወቅትም ‹‹ቅዱሳን ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስ እስኪወርድላቸው ድረስ በኢየሩሳሌም ከተማ እንዲቆዩ ታዝዘዋል፡፡ እኛም እግዚአብሔር ማስተዋሉን፣ ጥበቡንና ጸጋውን እንዲያድለን በቤተ ክርስቲያን መቆየት ይገባናል፤›› ብለዋል፡፡

እንደዚሁም ‹‹ወጣቱ ትውልድ ትኩስ ስለኾነ ኹሉም ነገር የሚጎዳ አይመስለውም፡፡ ክፉዉን ከበጎው ለመለየት የሚቻለን መንፈስ ቅዱስ ሲያድርብን ነው፡፡ መንፈስ ቅዱስ የሚያድርብን ደግሞ ሐቀኝነት፣ ፍቅር፣ ሰላም፣ እምነት፣ አንድነት ሲኖረን ነው፡፡ ጊዜውም መንፈስ ቅዱስ ለሐዋርያት የወረደበት ወቅት ነውና ራሳችንን ለመንፈስ ቅዱስ ማደሪያነት ማዘጋጀት ይገባናል፤›› ሲሉ አባታዊ ምክራቸውን አስተላልፈዋል፡፡

ቅዱስነታቸው አያይዘውም ‹‹ይህ ዓለም በብዙ ጣጣዎች የተሞላ ነውና በአገልግሎታችሁ ላይ ልዩ ልዩ ፈተና ሊመጣባችሁ ይችላል፡፡ በዚህ ጊዜ ፀላዔ ሠናያት ሰይጣንን ፃእ መንፈስ ርኵስ ማለት ያስፈልጋል፤›› ካሉ በኋላ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ለቤተ ክርስቲያን ሞገስ፣ ድምቀትና ተጨማሪ ሀብት መኾናቸውን ጠቅሰው ‹‹የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች ለቤተ ክርስቲያኒቱ ህልውና ስትሉ የምታነሡትን ጥያቄ ለመመለስ ዝግጁ ነን፤›› ሲሉ ቃል ገብተዋል፡፡

በመጨረሻም ‹‹ይህንን ሰላማዊ ጉባኤ በሰላም በማካሔዳችሁ ለደስታችን ወሰን የለውም፡፡ በዛሬው ዕለት በዚህ ጉባኤ ተገኝቼ ቡራኬ በመስጠቴ ደስታ ይሰማኛል፤›› ሲሉ ስሜታቸውን ገልጸዋል፡፡

የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ዋና ሓላፊ መ/ር ዕንቈባሕርይ ተከሥተ የመዝጊያ ንግግር ባደረጉበት ወቅት ለጉባኤው መሳካት አስተዋፅኦ ያደረጉ አካላትንና በጉባኤው የተገኙ የየሰንበት ት/ቤት ተወካዮችን ካመሰገኑ በኋላ ለየሀገረ ስብከቱ ሰ/ት/ቤት መምሪያዎች ፴፬ የመዝሙር ሲዲዎች በነጻ እንዲሠራጩ መደረጉን ገልጸው ‹‹ከእንግዲህ የመናፍቃንን ዘፈንና ቀረርቶ የምንሰማበት ጊዜ አይኖርም፡፡ ከዚህ በኋላ ኹላችንም ወደ ድጓው፣ ጾመ ድጓው ነው የምንሔደው!›› የሚል ቁጭት አዘል መልእክት አስተላልፈዋል፡፡

ሰኔ ፲ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ረፋድ ላይ በቅዱስ ፓትርያርኩ ጸሎተ ቡራኬ የተከፈተው ይህ የአንድነት ጉባኤ ባለ ፲፭ ነጥብ የጋራ የአቋም መግለጫውን በፓትርያርኩ ፊት ካቀረበ በኋላ በቅዱስነታቸው ቃለ ምዕዳንና ጸሎተ ቡራኬ ሰኔ ፲፪ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ከምሽቱ ፲፩ ተፈጽሟል፡፡

በጋራ የአቋም መግለጫውም፡- የተሐድሶ መናፍቃን የእምነት መግለጫ፣ የሰ/ት/ቤቶች በየቦታው መቋቋም፣ የአባላት የአገልግሎት ዘመን መሻሻል፣ የሰ/ት/ቤት ወጣቶች እንግልትና ስም የማጥፋት ዘመቻ፣ ወዘተ የመሳሰሉ ዐበይት ነጥቦች ተካተውበታል፡፡ የጉባኤውን ሙሉ የጋራ አቋም መግለጫ ተራ ቍጥሮችን፣ አንዳንድ ቃላትንና ፊደላትን አስተካክለን እንደሚከተለው አቅርበነዋል፤

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ የአገር አቀፍ የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ፭ኛ ዓመታዊ ጠቅላላ ጉባኤ የወጣ የጋራ አቋም መግለጫ

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃለ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፤

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ እና የወሊሶ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤

ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ እና የደቡባዊ ዞን የማይጨው፤ የምሥራቅ ትግራይ አዲግራትና መቐለ ዙሪያ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ የቅዱስ ሲኖዶስ አባል፤

ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ የበላይ ሓላፊ፤ የጉራጌ ስልጤ፣ ከምባታና ሐድያ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ የቅዱስ ሲኖዶስ አባል፤

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፤

የጠቅላይ ቤተ ክህነት የየመምሪያ ሓፊዎች፣ ጥሪ የተደረገላችሁ የክብር እንግዶች፤

እኛ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ጠቅላላ ጉባኤን ወክለን በ፭ኛው አገር አቀፍ የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት አጠቃላይ ጉባኤ ላይ የተሳተፍን የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ጠቅላላ ጉባኤ አባላት፣ ከሰኔ ፲-፲፪ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ላለፉት ሦስት ቀናት በማደራጃ መምሪያው ዓመታዊ የአገልግሎት ዘገባ፣ በ፳፭ አህጉረ ስብከት የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት እና የሰንበት ት/ቤቶች ዋና ክፍል የሥራ ክንውን ሪፖርት፤ እንደዚሁም የሰንበት ት/ቤቶች አባላት በኾኑ ባለሙያዎች በቀረቡ ሦስት ጥናታዊ ጽሑፎች ላይ ሰፊ ውይይት አድርገናል፡፡

የመምሪያው ዘገባም ኾነ ከ፳፭ አህጉረ ስብከት የመጡ ተወካዮች ያቀረቡት ሪፖርት ሰንበት ት/ቤቶች እጅግ በርካታ ተግባራት እያከናወኑ እንደሚገኙና የቤተ ክርስቲያንን ተልእኮ ለማፋጠን እየተጉ መኾናቸውን አስገንዝቧል፡፡

ኾኖም ግን በየአህጉረ ስብከቱ ያሉ መናፍቃን እና አፅራረ ቤተ ክርስቲያን ተጽዕኖዎች፣ በየአጥቢያ ሰንበት ት/ቤቶች እየደረሱ ያሉ የአስተዳደር በደሎች፣ የበጀት እና የመምህራን እጥረት፣ የመሰብሰቢያና የመማሪያ ቦታ አለመኖር፣ የአንዳንድ አህጉረ ስብከት ስፋት እና ለትራንስፖርት አመቺ አለመኾን አገልግሎቱን እየተፈታተኑ ያሉ ዋና ዋና ችግሮች ኾነው ተመዘግበዋል፡፡

በመጨረሻም በሪፖርቱም ኾነ በጥናታዊ ጽሐፎቹ የተጠቀሱትን ዋና ዋና ችግሮች በመለየት በተደረገው የጋራ ውይይት በቀጣይነት ሰንበት ት/ቤቶች በጋራ የምንሠራቸውን እና የምንስማማባቸውን የሚከተሉትን የአቋም መግለጫዎች አውጥተናል፤

፩.የሰ/ት/ቤቶች አንድነት የ፭ ዓመት ዕቅድ ማለትም ከ፳፻፮-፳፻፲ ዓ.ም ድረስ የታቀደውን መሪ ዕቅድ በቀሩት ጊዜያትም ለመፈጸምና ለማስፈጸም ቃል እንገባለን፡፡

፪.የሰ/ት/ቤቶች አጠቃላይ መሪ ዕቅድ የኹሉም አጥቢያ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ዕቅድ አካል እንዲኾን እና የጠቅላይ ቤተ ክህነት መምሪያዎችም የሰ/ት/ቤቶችን መሪ ዕቅድ ከዕቅዳቸው ጋር በማገናዘብ በዕቅድ እንዲካተቱ ይደረግ ዘንድ እንጠይቃለን፤

፫.መልክዓ ምድርን መሠረት ያደረገ የሰንበት ት/ቤቶች ትስስር በማጠናከር ሰንበት ት/ቤቶች ባልተቋቋሙባቸው አጥቢያዎች እንዲቋቋሙ፣ በተቋቋሙባቸው ደግሞ የተጠናከረ አገልግሎት እንዲሰጥባቸው ለማድረግ እንሠራለን፡፡

፬.በአገር አቀፍ ሰ/ት/ቤቶች አንድነት የተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴና መጠነ ሰፊ ጥፋትን አስመልክቶ በመረጃ ክፍል የተሰበሰቡና የተደራጁ ማስረጃዎችን ለቅዱስነትዎና ለቅዱስ ሲኖዶስ እንድናቀርብ እንዲፈቀድልን በአንድነት እንጠይቃለን፡፡

፭.በ፳፻፬ ዓ.ም በቅዱስ ሲኖዶስ የተወገዙ ፲፮ ግለሰቦችና ፰ ማኅበራት ያስተላለፏቸው የምንፍቅና ትምህርቶችና መጻሕፍት በሊቃውንት ጉባኤ መልስ እንዲሰጣቸው የታዘዘ ቢኾንም ነገር ግን እስከ ዛሬ ድረስ ምላሽ ባለመሰጠቱ ተሐድሶ ዘኦርቶዶክስ የእምነት መግለጫ የሚል የክህደት መግለጫ እስከ ማውጣት ደርሰዋል፡፡ ስለኾነም ለእነዚህ አካላት አስቸኳይ ምላሽ ይሰጥልን ዘንድ በአንድነት እንጠይቃለን፡፡

፮.በአሁኑ ሰዓት በቤተ ክርስቲያኒቷ ተልእኮ አፈጻጸም ላይ ተጽዕኖ እየፈጠረ ያለው የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ መናፍቃንን እንቅስቃሴ ለማስቆም ከቅዱስ ሲኖዶስ ጀምሮ በየደረጃው ያሉ የቤተ ክርስቲያን አካላት አፋጣኝ ርምጃ እንዲወስዱ እንጠይቃለን፡፡

፯.ከዚህ ቀደም በአዲስ አበባ ሰ/ት/ቤቶች የቀረበው የፕሮቴስንታዊ ተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴ መረጃ ውሳኔ እንዲሰጠው፤ ውሳኔው ተግባራዊ ይሆን ዘንድም ከቅዱስ ሲኖዶስ ጀምሮ ያሉ የቤተ ክርስቲያኒቷ አካላት አስፈላጊውን ርምጃ እንዲወስዱ እንጠይቃለን፡፡

፰.በአሁኑ ጊዜ በአንዳንድ የቤተ ክርስቲያን ሓላፊዎች በተሳሳተ አመክንዮ በሰንበት ት/ቤት ወጣቶች እና አባላት ላይ እየደረሰ ያለው እስር፣ እንግልት እና ወከባ እንዲቆምልን በአንጽዖት እንጠይቃለን፡፡

፱.ከዚህ ጋር ተያይዞ የመንግሥት የፍትሕ አካላትም ከአጥፊዎች ጋር በመተባበር የሰንበት ት/ቤት አባላትን ከማሰር እና ከማንገላታት እንዲታቀቡ እንዲደረግ በቅዱስ ሲኖዶስ በኩል መመሪያ እንሰጥልን እንጠይቃለን፡፡

፲.በቃለ ዓዋዲው እና በ፲፱፻፹፮ ዓ.ም በወጣው ውስጠ ደንብ ላይ የተጠቀሰው የሰ/ት/ቤቶች የዕድሜ ገደብ እንዲነሣልን በድጋሜ እንጠይቃለን፡፡

፲፩.ከሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ አንሥቶ እስከ አጥቢያ ሰ/ት/ቤቶች የሚደርስ የፋይናንስ ትስስር እና አያያዝ ሥርዓት በመምሪያው በኩል ተጠንቶ እንዲጸድቅልን እንጠይቃለን፡፡

፲፪.በዘመናችን ሚዲያ በወጣቱ እና በሕፃናት አስተዳደግ ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ እየፈጠረ ስለሚገኝ፣ የቤተ ክርስቲያኒቷን አስተምህሮ ለምእመናን በስፋት ማዳረስ እንዲቻል በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን የሚመራ እና የሚተዳደር፣ ቤተ ክርስቲያኒቷንም የሚወክል የቴሌቭዥን መርሐ ግብር ሥርጭት በመጀመሩ ከመምሪያው ጀምሮ እስከ አጥቢያ ያለን ሰንበት ት/ቤቶች አንድነት በጋራ ለመሥራት ቃል እንገባለን፡፡

፲፫.ተወካዮቻቸውን ያልላኩ አህጉረ ስብከት ተለይተው በጠቅላይ ቤተ ክህነት የማያዳግም ርምጃ እንዲወሰድባቸው እንጠይቃለን፡፡

፲፬.በቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊና ልማታዊ ጉዳዮች ከአባቶቻችን ጋር በመኾን ያለንን አቅም አሟጠን በመጠቀም ለቤተ ክርስቲያናችን ዕድገት እና ልዕልና የበኩላችንን ድርሻ እንወጣለን፡፡

፲፭.የቤተ ክርስቲያናችንን ኹለንተናዊ ችግሮች ለመፍታት ከመንፈሳዊ ኮሌጆች ምሩቃን ጋር ተባብረን የምንሠራ መኾናችንን እንገልጻለን፡፡

ሰኔ ፲፪ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም፡፡

በዓለ ጰራቅሊጦስ

ሰኔ ፲፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

*ጰራቅሊጦስ* የሚለው ቃል ከሦስቱ አካላት አንዱ ለኾነው ለእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ መጠሪያ ስሙ ሲኾን፣ ትርጕሙም በጽርዕ (ግሪክ) ቋንቋ ናዛዚ (የሚናዝዝ)፣ መጽንዒ (የሚያጸና)፣ መስተፍሥሒ (የሚያስደስት) ማለት ነው፡፡ በዓለ ጰራቅሊጦስ በሌላ ቃል በዓለ ጰንጠቆስጤ በመባልም ይታወቃል፡፡ ይኸውም በግሪክ ቋንቋ በዓለ ኀምሳ፣ የፋሲካ ኀምሳኛ ዕለት፣ በዓለ ሠዊት (የእሸት፣ የመከር በዓል) ማለት ነው /ኪዳነ ወልድ ክፍሌ፣ ገጽ ፱፻፮ እና ፱፻፯/፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ካረገ በኋላ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፣ ፲፪ቱ ደቀ መዛሙርት፣ ፸፪ቱ አርድእት፣ ፭፻ው ባልንጀሮችና ፴፮ቱ ቅዱሳት አንስት በኢሩሳሌም ከተማ በአንድነት ኾነው ለጸሎት ይተጉ ነበር፡፡ በሚያርግበት ጊዜም *እነሆ አባቴ የሰጠውን ተስፋ እኔ እልክላችኋለሁ፤ እናንተ ግን ከላይ ኃይል እስክትለብሱ ድረስ በኢየሩሳሌም ከተማ ቆዩ፤* /ሉቃ. ፳፬፥፵፱/ ሲል ለሐዋርያቱ በገባላቸው ቃል መሠረት ባረገ በ፲ኛው ቀን መንፈስ ቅዱስን ልኮላቸዋል፡፡

በሐዋርያት ሥራ እንደ ተጻፈው በበዓለ ጰራቅሊጦስ ማለዳ ኹሉም በአንድ ቦታ ተሰብስበው ሳሉ እንደ ዐውሎ ነፋስ ያለ ድምፅ ድንገት ከሰማይ መጣና የነበሩበትን ቤት ሞላው፡፡ ከዚያም እንደ እሳት የተከፋፈሉ የእሳት ላንቃዎች በኹሉም ላይ ተቀመጡባቸው፡፡ በዚህ ጊዜ ኹላቸውም መንፈስ ቅዱስን ከተሞሉ በኋላ መንፈስ ቅዱስ ባደላቸው መጠን በየአገሩ ቋንቋዎች ኹሉ መናገር ጀመሩ /ሐዋ.፪፥፩-፬/፡፡ ጌታችን መንፈስ ቅዱስን ለሐዋርያት የላከበት ይህ ዐቢይ በዓል ጰራቅሊጦስ ይባላል፡፡

ጌታችን ከሙታን ተለይቶ ከተነሣ ከ፶ኛው፤ ከዐረገ ከ፲ኛው ቀን ጀምሮ እስከሚቀጥለው እሑድ ድረስ ያለው ወቅትም ዘመነ ጰራቅሊጦስ ተብሎ የሚጠራ ሲኾን፣ ይህ በዓል ካህናተ ኦሪት ዐሥራቱን፣ በኵራቱን፣ ቀዳምያቱን ይቀበሉበት ነበርና በብሉይ ኪዳን በዓለ ሠዊት ይባል ነበር፡፡ በበዓለ ጰራቅሊጦስም ቅዱሳን ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስን ተቀብለውበታልና በበዓለ ሠዊት ምትክ በዓለ ጰራቅሊጦስ ገብቶበታል፡፡

የበዓለ ትንሣኤ መነሻው የአይሁድ የፋሲካ በዓል ማለትም በግብፅ እስራኤል ከሞት የዳኑበት የመታሰቢያ በዓል እንደ ኾነው ኹሉ፣ ለበዓለ ጰራቅሊጦስም መነሻው ይኸው የአይሁድ የፋሲካ በዓል ነው፡፡ የአይሁድ ፋሲካ ከተከበረ ከሰባት ሳምንታት በኋላ በ፶ኛው ቀን የሩቆቹ ከከተሙበት ወጥተው፣ የቅርቦቹ ከተሰባሰቡበት ተገናኝተው ለበዓሉ ፍጻሜ የሚኾነውን በዓለ ሠዊት ያከብሩ ነበር፡፡

ከግብፅ እስከ ከነዓን ምድር የደረሰው የእንስሳት መሥዋዕት ሲጠናቀቅ በ፶ኛው ቀን ይሰባሰብ የነበረው የአይሁድ ጉባኤም መንፈስ ቅዱስ ከወረደበት ዕለት ጀምሮ ተበትኗል፡፡ መሥዋዕተ ኦሪቱ በአማናዊው መሥዋዕት በኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋና ደም እንደ ተለወጠ ኹሉ ጉባኤ አይሁድም በኢየሩሳሌም ከተማ በተሰበሰቡ በቅዱሳን ሐዋርያት ጉባኤ ተለውጧል (ተቀይሯል)፡፡ ይህችውም ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ *ከኹሉ በላይ በምትኾን፣ ሐዋርያት በሰበሰቧት በአንዲት፣ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን እናምናለን፤* እንዳሉ ሠለስቱ ምእት /ጸሎተ ሃይማኖት/፡፡

ሐዋርያት በጽርሐ ጽዮን ተሰብስበው ሳሉ መንፈስ ቅዱስ በእሳት አምሳል ወርዶ ሰማያዊ ሀብትን፣ ዕውቀትና ጸጋን አድሏቸዋል፡፡ መንፈስ ቅዱስ ከወረደላቸው በኋላም በአእምሮ ጎልምሰዋል፤ ጥቡዓን (ቈራጦች)፣ ጽኑዓን ኾነዋል፤ ለስብከተ ወንጌል የሚፋጠኑበትንና ለሰማዕትነት የሚዘጋጁበትን ልቡና ታድለዋል፡፡ ቀድሞ ይናገሩት ከነበሩት ከዕብራይስጥ ቋንቋ በተጨማሪ ፸፩ ቋንቋዎች ተገልጸውላቸው ምሥጢራትን መተርጐም ጀምረዋል፡፡ ሐዋርያት በየገአሩ ቋንቋ ሲናገሩ የሰሙ ከአይሁድ ወገን አንዳንዶቹም ሐዋርያትን *ጉሽ ጠጅ ጠጥተው ሰክረው የኾነ ያልኾነውን ይቀባጥራሉ* ይሏቸው ነበር፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስም ይህንን ዐሳባቸውን በመንፈስ ቅዱስ አውቆ *ሰክረዋል የምትሉ እናንተ እንደምትጠራጠሩት አይደለም፡፡ ጊዜው ማለዳ፣ ሰዓቱም ገና ሦስት ሰዓት ነውና፡፡ ዳሩ ግን በነቢዩ ኢዩኤል ከዚህም በኋላ እንዲህ ይሆናል፤ መንፈሴን በሥጋ ለባሽ ሁሉ ላይ አፈስሳለሁ፤ ወንዶችና ሴቶች ልጆቻችሁም ትንቢት ይናገራሉ፤ /ኢዩ.፪፥፳፰/ ተብሎ የተነገረው ትንቢት ይፈጸም ዘንድ ይህንን ድንቅ ተአምር ያደረገው እናንተ የሰቀላችሁት ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፤* በማለት ሐዋርያት ኢየሱስ ክርስቶስ ነቢያት ትንቢት የተናገሩለት፣ ምሳሌ የመሰሉለት አምላክ ወልደ አምላክ መኾኑን፣ ከሙታን ተለይቶ መነሣቱን፣ ማረጉንና ዳግም በክብር በምስጋና መጥቶ በሕያዋንና በሙታን ላይ የሚፈረድ መኾኑን እንደሚመሰክሩ በአይሁድ ፊት አሰምቶ ተናገረ፡፡

በቅዱስ ጴጥሮስ ትምህርት የተማረኩ አሕዛብም *ምን እናድርግ* ብለው በጠየቁት ጊዜ ከክፋታቸው ተመልሰው፣ ንስሐ ገብተው በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እንዲጠመቁ ነገራቸው፡፡ በዚያችም ሰዓት ሦስት ሺህ ሕዝብ በኢየሱስ ክርስቶስ አምኖ ተጠምቋል /ሐዋ.፪፥፩-፵፩/፡፡ ይህም ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስ ከወረደላቸው በኋላ ያደረባቸው የማሳመን ጸጋና ተአምራትን የማድረግ ኃይላቸው እንደ በዛላቸው ያመላክታል፡፡

ይህ ዕለት ሀብተ መንፈስ ቅዱስ የተሰጠበት፤ ብዙ ሺሕ ምእመናን የተገኙበት ዕለት በመኾኑ ሊቃውንት የቤተ ክርስቲያን የልደት ቀን በማለት ይጠሩታል፡፡

ቅዱሳን ሐዋርያት *በዚህች ቀን በሦስት ሰዓት ኢየሱስ ክርስቶስ ጰራቅሊጦስን ልኮልናልና በላያችን ኃይልን ሞላ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ በሕያዋንና በሙታን ይፈርድ ዘንድ ሥልጣን እንዳለው በአዲስ ቋንቋ ተናገርን፤* በማለት በዕለቱ ያዩትንና የተደረገላቸውን፣ እንደዚሁም ስለ በዓሉ ታላቅነት ከመሰከሩ በኋላ ይህንን በዓል ማክበር እንደሚገባ አዝዘዋል፤ በአንጻሩ በዚህ ወቅት (በበዓለ ኀምሳ) መጾምና ማዘን ተገቢ አለመኾኑን ተናግረዋል /ዲድስቅልያ ፴፥፴፰-፴፱፤ ፴፩፥፷፱-፸/፡፡

የጰራቅሊጦስ መዝሙርና ምንባባት

በዓለ ጰራቅሊጦስ ከዘጠኙ የጌታችን ዐበይት በዓላት አንዱ ሲኾን በዕለቱ በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን የሚዘመረው የቅዱስ ያሬድ መዝሙርም ይትፌሣሕ የሚለው የትንሣኤ መዝሙር ነው፡፡ እንደ መዝሙሩ ኹሉ በጰራቅሊጦስ በዓል በቅዳሴ ጊዜ የሚነበቡ የቅዱሳት መጻሕፍት ክፍሎችም በትንሣኤ ዕለት የተነበቡት ምንባባት ናቸው፡፡

እነዚህም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ በመነሣቱ፣ በማረጉና መንፈስ ቅዱስን ለሐዋርያት በመላኩ፤ እንደዚሁም ሥጋውን ቈርሶ፣ ደሙን አፍስሶ የሰውን ልጅ ከዘለዓለም ሞት በማዳኑ የሰው ዘር ብቻ ሳይኾን የሰማይ መላእክት፣ የምድር ፍጥረታት ሳይቀሩ ሐሤት እንደሚያደርጉ፤ ምድርም በክርስቶስ ደም በመንጻቷ የጌታችንን ትንሣኤ በደስታ እንደምታከብር ያስረዳሉ፡፡

ከበዓለ ጰራቅሊጦስ በኋላ ባሉት ሰንበታት (እሑዶች) የሚዘመሩ መዝሙራት ትንሣኤን፣ ዕርገትን፣ የመንፈስ ቅዱስን መውረድ የሚያስረዱ ሲኾኑ፣ ዓላማቸውም ከሙታን ተለይቶ ለተነሣው፣ አዳምና ልጆቹን ከዲያብሎስ ባርነትና ከሲኦል ላወጣቸው ለልዑል እግዚአብሔር ምስጋና ማቅረብ ነው፡፡

ከዚሁ ኹሉ ጋር ለማሳሰብ የምንፈልገው ቁም ነገር በዓለ ጰራቅሊጦስን ተከትለው ሁለት ዐበይት አጽዋማት ይጀመራሉ፡፡ እነዚህም ጾመ ሐዋርያት እና ጾመ ድኅነት (ረቡዕና ዓርብ) ሲኾኑ፣ ቍጥራቸውም ከሰባቱ አጽዋማት ውስጥ ነው፡፡ ስለኾነም ኹላችንም ልንጾማቸው እንደሚገባ በቤተ ክርስቲያን ሕግ ታዝዟል፡፡ ይህም ከቀደሙ አባቶቻችን ጀምሮ የመጣ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ሥርዓት እንጂ እንግዳ ሕግ አይደለም፡፡

ቅዱሳት መጻሕፍት እንደሚናገሩት በብሉይ ኪዳን ነቢዩ ሙሴ ከእግዚአብሔር ዘንድ የተቀበለውን ሕገ ኦሪት ለሕዝቡ ከማስተማሩ በፊት ጾሟል /ዘፀ.፴፬፥፳፰/፡፡ ቅዱሳን ነቢያትም የተስፋውን ቃል መፈጸም እየተጠባበቁ እግዚአብሔርን ውረድ፤ ተወለድ እያሉ ይጾሙ፣ ይጸልዩ ነበር፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ጾም የምግባር መሠረት መኾኑን ሊያስተምረን ወንጌልን ከመስበኩ አስቀድሞ ጾሟል /ማቴ.፬፥፩-፲፩/፤ ሐዋርያትም በበዓለ ኀምሳ መንፈስ ቅዱስ ከወረደላቸው በኋላ ሕገ ወንጌልን ለሕዝቡ ከማስተማራቸው አስቀድሞ ጾመዋል፡፡

እኛም እነርሱን ተከትለን፣ በእነርሱ ሥርዓት በመመራት፣ በሐዋርያት ላይ ያደረው የመንፈስ ቅዱስ ጸጋና ሀብት በእኛም ላይ እንዲያድርብን በየዓመቱ ጾመ ሐዋርያትንና ሌሎችንም አጽዋማት መጾም እንደሚገባን በቀኖና ቤተ ክርስቲያን ተወስኗል /ፍት.ነገ. ፲፭፥፭፹፮/፡፡

ጾመ ድኅነት ስሙ እንደሚያመለክተው የመዳን ጾም ማለት ሲኾን፣ ይህም በብሉይ ኪዳኑ አጽዋማት በጾመ አስቴር እና በጾመ ዮዲት የተተካ የሐዲስ ኪዳን ጾም ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን በሐማ ምክንያት በእስራኤል ላይ ታውጆ የነበረው ሞት በጾመ አስቴር እንደ ተሻረ ኹሉ፣ በሐዲስ ኪዳንም በዕለተ ረቡዕ በጌታችን ላይ በተፈጸመው ምክር የሰይጣን ሴራ ፈርሷልና በጾመ አስቴር ምትክ ረቡዕን እንጾማለን፡፡

እንደዚሁም በብሉይ ኪዳን በጾመ ዮዲት ምክንያት ሆሎሆርኒስ ድል እንደ ተደረገበት ኹሉ፣ በሐዲስ ኪዳንም መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕለተ ዓርብ በመስቀል ላይ በከፈለው መሥዋዕትነት ዲያብሎስ ድል ተደርጓልና በጾመ ዮዲት ምትክ ዓርብን እንጾማለን፡፡ የእነዚህ የሁለቱ ቀናት (የረቡዕና ዓርብ) ጾም ጾመ ድኅነት ይባላል፡፡

በአጠቃላይ ጾመ ሐዋርያትና ጾመ ድኅነት እንደ ጾመ ነነዌና ዐቢይ ጾም የበዓላትና የአጽዋማት ማውጫ ቀመርን ተከትለው የሚመጡ ከሰባቱ አጽዋማት መካከል የሚመደቡ ጾሞች ናቸው፡፡ የጾመ ሐዋርያት ፋሲካ (መፈጸሚያ) የቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ጳውሎስ በዓለ ዕረፍት (ሐምሌ ፭ ቀን) ሲኾን፣ ጾመ ድኅነት ግን ከበዓለ ኀምሳ በስተቀር ዓመቱን ሙሉ የሚጾም ጾም ነው፡፡

ዕለተ ረቡዕ የጌታ ሞት የተመከረበት፤ ዓርብም አምላካችን የተሰቀለበት ዕለት ነውና በመስቀሉ መሥዋዕትነት ያገኘውን ድኅነት ዘወትር ማሰብ ስለሚገባን ሁልጊዜ እንድንጾማቸው በቅዱስ ሲኖዶስ ሥርዓት ተሠርቶልናል፡፡ በዚህ ዓመት ጾመ ሐዋርያት ሰኔ ፲፫፤ ጾመ ድኅነት ደግሞ ሰኔ ፲፭ ቀን ይጀመራሉ፡፡ በመኾኑም እንደ ክርስቲያን የምንጠቀመው በራሳችን መልካም ተግባር፤ የምንወቀሰውም በራሳችን መጥፎ ድርጊት መኾኑን ተረድተን ይኼ የቄሶች፤ ይኼ የመነኰሳት ነው የሚል ሰበብ ሳንፈጥር ኹላችንም በአንድነት ብንጾማቸው ከእግዚአብሔር ዘንድ የምናገኘው ጸጋና ሀብት ይበዛልናልና ራሳችንን ለጾም እናዘጋጅ፡፡

በዓለ ትንሣኤውን በደስታ እንድናሳልፍ ፈቅዶ እስከ ዛሬ ድረስ እንዳቆየን፣ አሁን ደግሞ በጾም፣ በጸሎት ኾነን እርሱን የምናመሰግንበትን ወቅት ስላመጣልን አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር ስሙ ለዘለዓለሙ የተመሰገነ ይኹን፡፡

ምንጭ፡-

መጽሐፈ ስንክሳር፣ ግንቦት ፲፰ ቀን፡፡

መጽሐፈ ግጻዌ ዘደብር ዓባይ፣ ሊቀ ሥልጣናት አባ ጥዑመ ልሳን፤ አዲስ አበባ፣ ፳፻፩ ዓ.ም፡፡

መዝገበ ታሪክ፣ ክፍል ፪፣ ገጽ ፹፬-፹፭፣ መ/ር ኅሩይ ኤርምያስ፣ ፲፱፻፺፭ ዓ.ም፡፡

ማኅቶተ ዘመን ገጽ ፻፺፭-፪፻፬፣ መ/ር በሙሉ አስፋው፤ ፳፻፩ ዓ.ም፡፡

የደቡብ ማእከላት የአንድነት ጉባኤ አካሔዱ፡፡

ሰኔ ፲ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በሐዋሳ ማእከል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን በሐዋሳ ማእከል አዘጋጅነት በደቡብ ማስተባበሪያ ሥር ያሉት የዘጠኝ ማእከላት ሥራ አስፈጻሚዎችና አባላት ከሰኔ ፫-፭ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ድረስ በሐዋሳ ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን የግቢ ጉባኤ አዳራሽ የልምድ ልውውጥና የአንድነት ጉባኤ አካሔዱ፡፡

በዕለቱ የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጸሐፊ አቶ ተስፋዬ ቢኾነኝ፣ እንዲሁም የማኅበረ ቅዱሳን ሥራ አመራር አባል አቶ ፋንታኹን ዋቄ የተገኙ ሲኾን፣ በመርሐ ግብሩ መክፈቻ ላይም የነቃህ ኹን /ራእ.፫፥፪/ በሚል ኃይለ ቃል ወቅታዊውን የቤተ ክርስቲያን አገልግሎትና ሓላፊነትን መሠረት ያደረገ ትምህርተ ወንጌል በዲያቆን ስንታየሁ ጂሶ ተሰጥቷል፡፡ በጉባኤውም ፺ የየማእከላት ሥራ አስፈጻሚ ጉባኤና የሐዋሳ ማእከል አባላት ተሳትፈዋል፡፡

በጉባኤው ሁለተኛ ቀን የቤተ ክርስቲያንን ኹለንተናዊ አገልግሎት ለመደገፍ የማኅበረ ቅዱሳንን ድርሻ የሚያመለክት ሥልጠና በማኅበሩ ዋና ጸሐፊ አቶ ተስፋዬ ቢኾነኝ የተሰጠ ሲኾን፣ በልምድ ልውውጡ መርሐ ግብርም መልካም አርአያነት ያላቸው ማእከላትና ንዑሳን ክፍሎች የልምድ ተሞክሯቸውን ለጉባኤው ተሳታፊዎች አካፍለዋል፡፡

እንደዚሁም በደቡብ ማእከላት ማስተባበሪያ ጽ/ቤት ሓላፊ በመ/ር ዘሪሁን ከበደ የዘጠኙም ማእከላት የአራት ዓመት የማኅበረ ቅዱሳን ስልታዊ ዕቅድ አፈጻጸም ማጠቃለያ የቀረበ ሲኾን፣ በተጨማሪም በጉባኤው ፫ኛ ቀን ውሎ፣ Living the Orthodx Life in the Era of Globalization and Secular Humanism፤ ኦርቶዶክሳዊ ሕይወት በዘመነ ሉላዊነትና ዓለማዊነት በሚል ርእስ በአቶ ፈንታሁን ዋቄ የግማሽ ቀን ሥልጠና ተሰጥቷል፡፡

በመጨረሻም የደቡብ ማእከላት ማስተባበሪያ ጽ/ቤት ሓላፊ ይህ ጉባኤ ለየማእከላቱ አገልግሎት መነሣሣት የሚኖረውን አስተዋጽኦ ከገለጹና የ፳፻፱ ዓ.ም ተመሳሳይ ጉባኤ አዘጋጅ ወላይታ ዶ ማእከል እንዲሆን ከተወሰነ በኋላ ሰኔ ፭ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ከምሽቱ ፭ ሰዓት የአንድነት ጉባኤው ተፈጽሟል፡፡

በጅማ ሀገረ ስብከት በምእመናን ላይ በደረሰው ጉዳት ማኅበረ ቅዱሳን አዝኗል

ሰኔ ፱ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዝግጅት ክፍሉ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን በጅማ ሀገረ ስብከት የም ልዩ ወረዳ ቁንቢ ቀበሌ ሰኔ ፰ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በምእመናን ላይ በደረሰው ጉዳት በእጅጉ ማዘኑን ገለጸ፡፡

አቶ ተስፋዬ ቢኾነኝ የማኅበሩ ዋና ጸሐፊ ‹‹ስለ ኹኔታው የሚደረገው የማጣራት ሥራ እንደ ተጠበቀ እና ወደፊት የሚገለጽ ኾኖ፣ አጥቂዎቹ በወገኖቻችን ላይ ያደረሱት ጉዳት በእጅጉ የሚያሳዝን፤ ሊወገዝ የሚገባው ድርጊትም ነው፡፡ ይህንን ድርጊት የፈጸሙት ሰዎች አካሔዳቸው በየትኛውም የእምነት መሥፈርት፣ ይልቁንም በክርስትና አስተምህሮ ከመንፈሳዊ እምነትና ዓላማው ውጪ ነው›› ሲሉ ተናግረዋል፡፡

ዋና ጸሐፊው አያይዘውም ‹‹ክርስትና የመስቀል ጉዞ እንደ መኾኑ ብዙ ፈተና አለው፡፡ እምነታችን እስከ ዛሬ ድረስ የቆየውም በደማቸው ሰማዕት ኾነው ባለፉ አበውና እማት ተጋድሎ ነው፡፡ በመኾኑም ምእመናን ይህንን ተረድተው በጉዳዩ መደናገጥ የለባቸውም፡፡ ማኅበራችንም በተደጋጋሚ ጉዳት እየደረሰበት ያለውን የጅማ ሀገረ ስብከት ከሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ከብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ ጋር በመተባበር እና መመሪያቸውንም በመቀበል በተቻለው ኹሉ ድጋፍ ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ ወደፊትም ድጋፉን ይቀጥላል›› ብለዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ የጅማ፣ የኢሉባቡርና የጋምቤላ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ከዝግጅት ክፍላችን ጋር በስልክ ባደረጉት ቃለ ምልልስ በምእመናን ላይ በደረሰው ጉዳት ማዘናቸውን ገልጸው፣ ከሀገረ ስብከቱ፣ ከእስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት፣ ከፌዴራልና ከክልሉ መንግሥት በተመረጡ አባላት የተዋቀረ ኰሚቴ ጉዳዩን እያጣራ መኾኑን አስረድተዋል፡፡ የኰሚቴውን የምርመራ ውጤትም በሀገረ ስብከታቸው በኩል ለሕዝበ ክርስቲያኑና ለዝግጅት ክፍላችን ይፋ እንደሚያደርጉ ብፁዕነታቸው አስታውቀዋል፡፡

በአጥቂዎች ጉዳት የደረሰባቸው ሁለት እኅትማማች ምእመናት በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል የሕክምና ርዳታ እየተደረገላቸው ሲኾን፣ በትናንትናው ዕለት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ከብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ጋር በመኾን በሆስፒታሉ ተገኝተው ጉዳት የደረሰባቸውን ምእመናትና ቤተሰቦቻቸውን ማጽናናታቸው ይታወሳል፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን ቴሌቭዥንና ሬድዮ ሥርጭቶች ብዙ አድማጭ ተመልካች እንዳላቸው ተጠቆመ፡፡

ሰኔ ፱ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

በማኅበረ ቅዱሳን ኅትመትና ኤሌክትሮኒክስ ሚድያ ዋና ክፍል በብሮድካስት ሚድያ ክፍል ተዘጋጅተው በየሳምንቱ የሚተላለፉት የማኅበረ ቅዱሳን የቴሌቭዥንና ሬድዮ ሥርጭቶች ከፍተኛ ተመልካችና አድማጭ እንዳላቸው ተጠቆመ፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን የብሮድካስት ሚድያ ክፍል ምክትል ዳይሬክተር የኾኑት ዲ/ን ቴዎድሮስ ኃይሉ፤ ማኅበረ ቅዱሳን ከተመሠረተበት ጊዜ ጀምሮ በኅትመት ውጤቶች (ሐመር መጽሔትና ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ) በመታገዝ በመላው ዓለም ለሚገኙ ምእመናን መንፈሳዊ ትምህርት ሲሰጥ መቆየቱን፤ እንደዚሁም ከ፲፱፺፯ ዓ.ም ጀምሮ በሬድዮ፣ ከ፳፻፭ ዓ.ም ጀምሮ ደግሞ በቴሌቭዥን መርሐ ግብር አገልግሎቱን በማፋጠን ላይ እንደሚገኝ አውስተዋል፡፡

በአኹኑ ሰዓትም ዘወትር እሑድና ሐሙስ በኢቢኤስ የቴሌቭዥን ጣቢያ ይቀርብ የነበረው የአንድ ሰዓት መርሐ ግብር አገር ውስጥ በቀጥታ ባይተላለፍም፣ በአሜሪካን አገር በበርካታ ግዛቶች በማኅበረሰብ ቴሌቭዥን በመተላለፍ ላይ እንደሚገኝ፤ በአገር ውስጥና በሌሎች የዓለም ክፍሎች ለሚገኙ ተመልካቾች ደግሞ ለዚሁ ተብሎ በተዘጋጀው ድረ ገጽ ላይ በሰፊው እየታየ መኾኑን ዲ/ን ቴዎድሮስ ጨምረው ገልጸዋል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ምእመናን የቤተ ክርስቲያናቸውን ትምህርት በስፋት ያገኙ ዘንድ በአማርኛ ቋንቋ ከሚያስተላልፈው ከሁለት ሰዓታት የኢንተርኔት ቴሌቭዥን ዝግጅት በተጨማሪ ለኦሮምኛ ቋንቋ ተናጋሪ ምእመናን በየሳምንቱ እሑድ ከረፋዱ 4፡30-5፡00 በኦቢኤስ አማካይነት በአፋን ኦሮሞ ልዩ ልዩ ዝግጅቶችን እንደሚያስተላልፍ የጠቀሱት ዲ/ን ቴዎድሮስ፣ ኹሉም የማኅበሩ ዝግጅቶች በመላው ዓለም ብዙ ተመልካቾችና አድማጭች እንዳሏቸው በየጊዜው ከሚያደርጓቸው የዳሰሳ ጥናቶች መረዳታቸውንም ተናግረዋል፡፡

አያይዘውም ከቴሌቭዥን ዝግጅቶቹ በተጨማሪ የቤተ ክርስቲያኗ ትምህርተ ሃይማኖትና ሥርዓተ እምነት እንዲሁም ልዩ ልዩ መንፈሳዊ ጉዳዮች የሚቀርቡበት ሳምንታዊ የሬድዮ መርሐ ግብር መኖሩንም ተናግረዋል፡፡

በተጨማሪም የማኅበሩ የየሳምንቱ የሬድዮና የቴሌቪዥን ዝግጅቶች Radio/Tv by Phone በሚል መርሐ ግብር በልዩ ልዩ የዓለም ክፍሎች በመሠራጨት ላይ እንደሚገኙ፤ እነዚህን መርሐ ግብሮችም አሜሪካ፡- በ(605)475-8172፤ ጀርመን፡- በ+49699.432.98.11፤ ዩናይትድ ኪንግደም፡- በ+4433.0332.63.60፤ ካናዳ፡- በ(604) 670-9698 ላይ ስልክ በመደወል መከታተል እንደሚቻል ዲ/ን ቴዎድሮስ የሰሜን አሜሪካ ማእከል የላከውን ምንጭ ጠቅሰው ጠቁመዋል፡፡

በአጠቃላይ ኹሉንም የማኅበረ ቅዱሳን የሬድዮና ቴሌቭዥን መርሐ ግብሮች በwww.eotc.tv እና በfacebook አድራሻ mahiberekidusan.mkusa መከታተል እንደሚቻል ዝግጅት ክፍሉ አስታውቋል፡፡

የጎንደር ማእከል ፮ኛውን የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር አካሔደ፡፡

ሰኔ ፱ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በጎንደር ማእከል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን ጎንደር ማእከል ግንቦት ፳፰ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ፮ኛውን የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር በደንቢያ ወረዳ በግራርጌ መካነ ሕይወት አባ ሊባኖስ ቤተ ክርስቲያን አካሔደ፡፡

በመርሐ ግብሩ ላይም ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ የአካባቢው ምእመናን፣ የየወረዳ ማእከላት አባላት፣ የደንቢያ ከተማ መንፈሳውያን ማኅበራት እና የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች የተገኙ ሲኾን፣ በአጠቃላይ የአካባቢውን ማኅበረሰብ ጨምሮ ከ፲፭፻ በላይ ምእመናን በጉባኤው ተሳትፈዋል፡፡ በዕለቱ በተደረገው ጉባኤም በጎንደር ማእከል የመዝሙርና የኪነ ጥበባት ክፍል አባላት መዝሙርና መንፈሳዊ ሥነ ጽሑፍ ቀርቧል፡፡

በጠዋቱ መርሐ ግብር የቤተ ክርስቲያኑ ታሪክ በአስተዳዳሪው ከተነገረ በኋላ እጅግ ጠቢብ አትሁን /ጥበ.፯፥፲፯/ በሚል ኃይለ ቃል በዲ/ን ብርሃኑ አድማስ ትምህርተ ወንጌል የቀረበ ሲኾን፣ በመቀጠልም የአብርሃም ቤት እንግዳ ተጋባዥ የኾኑት በማኅበረ ቅዱሳን ቅዱሳት መካናት እና ገዳማት ክፍል ምክትል የቦርድ ሰብሳቢ ወ/ሮ ዓለም ፀሐይ መሠረት ስለ ማኅበረ ቅዱሳን አመሠራረትና እስከ ዛሬ ድረስ ስላለው የአገልግሎት ኹኔታ ሰፋ ያለ ገለጻ በማድረግ የሕይወት ተሞክሯቸውን አካፍለዋል፡፡

በተጨማሪም ማኅበረ ቅዱሳን ለገዳማት፣ ለአብያተ ክርስቲያናት እና ለአብነት ትምህርት ቤቶች እያደረገ ያለውን አስተዋጽኦ ተናግረዋል፡፡

ከሰዓት በቀጠለው መርሐ ግብርም በደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት በደብረ ሃይማኖት መካነ ኢየሱስ የመጻሕፍት ጉባኤ ቤት ደቀ መዝሙር የኾኑት አባ ገብረ ኪዳን ግርማ መንግሥተ ሰማያት በመካከላችሁ ናት /ሉቃ.፲፯፥፳፩/ በሚል ኃይለ ቃል ትምህርተ ወንጌል ከሰጡ በኋላ ሰባኬ ወንጌል ዋኬ ጉንዳ በቤንሻንጉል ጉምዝ ክልል በመተከል ሀገረ ስብከት ዙሪያ ያለውን የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ኹኔታ ለጉባኤው ተሳታፊዎች አቅርበዋል፡፡

ሰባኬ ወንጌል ዋኬ አያይዘውም የመተከል ሀገረ ስብከት የሰባክያነ ወንጌል፣ የአገልጋይ ካህናትና የሕንፃ አብያተ ክርስቲያናት እጥረት ያለበት አካባቢ መኾኑን ጠቅሰው ምእመናኑ ቃለ እግዚአብሔርን ለተራቡ ለአካባቢው ወገኖች ሰፊ እገዛ እንዲያደርጉ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡

በዕለቱ በወጣትነት እና ክርስትና፣ በክርስቲያናዊ አለባበስ፣ በፈቃደ እግዚአብሔር፣ በ፵ ቀን ዕድል፣ በካህኑ መልከ ጼዴቅ የዘር ሐረግ፣ ለአብርሃም በተገለጹት ሥላሴ ዙሪያ ከምእመናን የተነሡ ጥያቄዎች በዲ/ን ብርሃኑ አድማስ ሰፊ ምላሽ ተሰጥቶባቸዋል፡፡

የማእከሉ ሰብሳቢ መምህር ዓለማየሁ ይደግ ንግግር ባደረጉበት ወቅት እንዲህ አይነት መርሐ ግብራት መዘጋጀታቸው በዓለም የባዘኑትን ምእመናን ሕይወት ለመለወጥ ትልቅ ድርሻ እንዳላቸው የገለጹ ሲኾን፣ በመርሐ ግብሩ የተሳተፉ ምእመናንም ጉባኤው አእምሯቸውን ያጎለመሱበት፣ መንፈሳቸውን ያደሱበት፣ ሕይወታቸውን የተፈተሹበትና የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ የተረዱበት መኾኑን ገልጸው እንደዚህ ዓይነቱ መርሐ ግብር ለወደፊቱ በዓመት ሦስት አራት ጊዜ ቢዘጋጅ ሲሉ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡

በመጨረሻም ለቤተ ክርስቲያኑ ገቢ የሚሆን ገንዘብ ከጉባኤው ተሳታፊዎች ከተሰበሰ በኋላ መርሐ ግብሩ በአባቶች ጸሎትና ቡራኬ ተጠናቋል፡፡