የማኅበረ ቅዱሳን ቴሌቭዥንና ሬድዮ ሥርጭቶች ብዙ አድማጭ ተመልካች እንዳላቸው ተጠቆመ፡፡

ሰኔ ፱ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

በማኅበረ ቅዱሳን ኅትመትና ኤሌክትሮኒክስ ሚድያ ዋና ክፍል በብሮድካስት ሚድያ ክፍል ተዘጋጅተው በየሳምንቱ የሚተላለፉት የማኅበረ ቅዱሳን የቴሌቭዥንና ሬድዮ ሥርጭቶች ከፍተኛ ተመልካችና አድማጭ እንዳላቸው ተጠቆመ፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን የብሮድካስት ሚድያ ክፍል ምክትል ዳይሬክተር የኾኑት ዲ/ን ቴዎድሮስ ኃይሉ፤ ማኅበረ ቅዱሳን ከተመሠረተበት ጊዜ ጀምሮ በኅትመት ውጤቶች (ሐመር መጽሔትና ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ) በመታገዝ በመላው ዓለም ለሚገኙ ምእመናን መንፈሳዊ ትምህርት ሲሰጥ መቆየቱን፤ እንደዚሁም ከ፲፱፺፯ ዓ.ም ጀምሮ በሬድዮ፣ ከ፳፻፭ ዓ.ም ጀምሮ ደግሞ በቴሌቭዥን መርሐ ግብር አገልግሎቱን በማፋጠን ላይ እንደሚገኝ አውስተዋል፡፡

በአኹኑ ሰዓትም ዘወትር እሑድና ሐሙስ በኢቢኤስ የቴሌቭዥን ጣቢያ ይቀርብ የነበረው የአንድ ሰዓት መርሐ ግብር አገር ውስጥ በቀጥታ ባይተላለፍም፣ በአሜሪካን አገር በበርካታ ግዛቶች በማኅበረሰብ ቴሌቭዥን በመተላለፍ ላይ እንደሚገኝ፤ በአገር ውስጥና በሌሎች የዓለም ክፍሎች ለሚገኙ ተመልካቾች ደግሞ ለዚሁ ተብሎ በተዘጋጀው ድረ ገጽ ላይ በሰፊው እየታየ መኾኑን ዲ/ን ቴዎድሮስ ጨምረው ገልጸዋል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ምእመናን የቤተ ክርስቲያናቸውን ትምህርት በስፋት ያገኙ ዘንድ በአማርኛ ቋንቋ ከሚያስተላልፈው ከሁለት ሰዓታት የኢንተርኔት ቴሌቭዥን ዝግጅት በተጨማሪ ለኦሮምኛ ቋንቋ ተናጋሪ ምእመናን በየሳምንቱ እሑድ ከረፋዱ 4፡30-5፡00 በኦቢኤስ አማካይነት በአፋን ኦሮሞ ልዩ ልዩ ዝግጅቶችን እንደሚያስተላልፍ የጠቀሱት ዲ/ን ቴዎድሮስ፣ ኹሉም የማኅበሩ ዝግጅቶች በመላው ዓለም ብዙ ተመልካቾችና አድማጭች እንዳሏቸው በየጊዜው ከሚያደርጓቸው የዳሰሳ ጥናቶች መረዳታቸውንም ተናግረዋል፡፡

አያይዘውም ከቴሌቭዥን ዝግጅቶቹ በተጨማሪ የቤተ ክርስቲያኗ ትምህርተ ሃይማኖትና ሥርዓተ እምነት እንዲሁም ልዩ ልዩ መንፈሳዊ ጉዳዮች የሚቀርቡበት ሳምንታዊ የሬድዮ መርሐ ግብር መኖሩንም ተናግረዋል፡፡

በተጨማሪም የማኅበሩ የየሳምንቱ የሬድዮና የቴሌቪዥን ዝግጅቶች Radio/Tv by Phone በሚል መርሐ ግብር በልዩ ልዩ የዓለም ክፍሎች በመሠራጨት ላይ እንደሚገኙ፤ እነዚህን መርሐ ግብሮችም አሜሪካ፡- በ(605)475-8172፤ ጀርመን፡- በ+49699.432.98.11፤ ዩናይትድ ኪንግደም፡- በ+4433.0332.63.60፤ ካናዳ፡- በ(604) 670-9698 ላይ ስልክ በመደወል መከታተል እንደሚቻል ዲ/ን ቴዎድሮስ የሰሜን አሜሪካ ማእከል የላከውን ምንጭ ጠቅሰው ጠቁመዋል፡፡

በአጠቃላይ ኹሉንም የማኅበረ ቅዱሳን የሬድዮና ቴሌቭዥን መርሐ ግብሮች በwww.eotc.tv እና በfacebook አድራሻ mahiberekidusan.mkusa መከታተል እንደሚቻል ዝግጅት ክፍሉ አስታውቋል፡፡