የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን Encyclopedia ዝግጅት መጀመሩ ተበሠረ፡፡

ሰኔ ፯ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

የማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማእከል ሰኔ ፬ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ከረፋዱ 5፡45 ጀምሮ ከቤተ ክርስቲያን ሊቃውንትና የዩኒቨርሲቲ ምሁራን ጋር በአዲስ አበባ ከተማ በሰሜን ሆቴል አዳራሽ ባደረገው ውይይት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን Encyclopedia (በጊዜያዊ ትርጕሙ ባሕረ ጥበባት) ዝግጅት በይፋ መጀመሩ ተበሠረ፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን ምክትል ዋና ጸሐፊ አቶ ሰይፈ ዓለማየሁ የመክፈቻ ንግግር ባደረጉበት ወቅት እንደ ገለጹት ማኅበረ ቅዱሳን በዕቅድ ከሚሠራቸው ዐበይት ተግባራት መካከል ይህ በማኅበሩ ጥናትና ምርምር ማእከል የሚሠራው የEncyclopedia ዝግጅት አንዱ መኾኑን ጠቅሰው ለዚህ ተግባር መሳካት አስተዋጽኦ በማድረግ ላይ የሚገኙትን ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና የዩኒቨርሲቲ ምሁራን አመስግነዋል፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማእከል ዳይሬክተር ዶ/ር አባተ መኩሪያው የማእከሉን ዓላማ ለጉባኤው ባቀረቡበት ወቅት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የብዙ ሀብት ምንጭ፣ የጥንታውያን ቅርሶች ባለቤትና የብዙ ሺሕ ምእመናን መገኛ ኾና ሳለ እስከ አሁን ድረስ Encyclopedia ሳይኖራት መቆየቷ ለቤተ ክርስቲያን ብቻ ሳይኾን ለአገርም ክፍተት የሚፈጥር መኾኑን ገልጸው የማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማእከል ይህንን ችግር ግምት ውስጥ በማስገባትና የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ለትውልድ ለማስተላለፍ ይቻል ዘንድ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመመካከር ባሕረ ጥበባት ለማዘጋጀት መወሰኑን አብሥረዋል፡፡

የዝግጅት ሥራውን በተመለከተ የEncyclopedia ዝግጅቱ በብፁዕ አቡነ ሉቃስ ሊቀ ጳጳስ የሚመራ የአማካሪ ቦርድ፣ እንደዚሁም የአርትዖት ክፍል አባላት እንዳሉትና በዝግጅቱም ከሦስት መቶ ሰባት ባላይ የአገር ውስጥና የውጭ አገር ባለሙያዎች እንደሚሳተፉበት ዶ/ር አባተ ጨምረው ገልጸዋል፡፡

ከአማካሪ ቦርድ አባላት መካከል አንዱ የኾኑት መልአከ ታቦር ተሾመ ዘሪሁን በዕለቱ አስተያየት ሲሰጡ የአንድ ሺሕ ኪሎ ሜትር ጉዞ በአንድ ርምጃ ይጀምራል የሚለውን ብሂል ጠቅሰው ይህ የባሕረ ጥበባት ዝግጅትም ጥሩ ጅማሬ ነውና እንደ ጥሩ ፍጻሜ ይቈጠራል ብለዋል፡፡ ሥራው ብዙ ፈተናና ድካም እንደሚኖረው የተናገሩት መልአከ ታቦር እኛ ከማለፋን በፊት ጅማሬውን ብናየው ደስ ይለናል ካሉ በኋላ አቋራጭ መንገዶችን በመጠቀም በቅርቡ ለንባብ እንዲበቃ ጥረት ማድረግ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡ Encyclopedia ከሚለው ቃል ትርጕም አኳያም መድበል የሚለው ቃል በትርጕሙ ውስጥ ቢካተት የተሻለ መኾኑን ጠቅሰዋል፡፡

ሌላው የአማካሪ ቦርድ አባል ቀሲስ ዶ/ር ምክረ ሥላሴ ገብረ አማኑኤል በበኩላቸው ለዚህ ሥራ እዚህ ደረጃ ላይ መድረስ ጥረት ሲያደርግ የቆየውን ማኅበረ ቅዱሳንን አመስግነው የቤተ ክርስቲያን Encyclopedia እስከ አሁን ድረስ አለመዘጋጀቱ ቢያስቈጭም እኛ ግን መቀመጥ የለብንም ብለዋል፡፡ አያይዘውም Encyclopedia የሚለው ቃል ከግሪክ ቋንቋ የተወሰደና ትርጕሙም የጥበብ (የዕውቀት) መገኛ (ስብስብ) ማለት መኾኑን ጠቅሰው ባሕረ ጥበባት ከሚለው ትርጕም በበለጠ ሊገልጸው የሚችል አቻ ትርጕም ሊሰጠው እንደሚገባ ጠቁመው እንደ መነሻም መዝገበ አእምሮ፣ መዝገበ ጥበባት ወይም ፈለገ አእምሮ፣ ፈለገ ጥበባት፣ ወዘተ በሚል ቢተረጐም የሚል ዐሳብ ሰጥተዋል፡፡

ሌሎች የአማካሪ ቦርዱ እና የአርትዖት ክፍሉ አባላትም አስተያየት በሰጡበት ወቅት በዝግጅቱ መጀመርና የዝግጅቱ አባላት በመኾቸው የተሰማቸውን ደስታ ገልጸው ይህ ሥራ በሚሠራበት ጊዜ ልዩ ልዩ ፈተናዎችና ነቀፋዎች ሊያጋጥሙ እንደሚችሉ ከወዲሁ በመረዳት ኹሉንም ነገር ለበጎ መኾኑን ማስተዋልና ችግሮችንም በትዕግሥት ማለፍ አስፈላጊ መኾኑን ተናግረዋል፡፡ ለዚህም እግዚአብሔርን በጸሎት መጠየቅ እንደሚገባ ለራሳቸውም ለሌሎች የዝግጅቱ አባላትም አባታዊና ወንድማዊ ምክራቸውን ለግሰዋል፡፡

በውይይቱ ማጠቃለያም የአማካሪ ቦርድ እና የአርትዖት ክፍል ሥራ አስፈጻሚ ኰሚቴ የተዋቀረ ሲኾን፣ በዚህ መሠረት ለአማካሪ ቦርዱ፡- ፕ/ር ሽፈራው በቀለ ሰብሳቢ፣ ፕ/ር ባየ ይማም ምክትል ሰብሳቢ፣ ዶ/ር አባተ መኩሪያው ጸሐፊ፤ ለአርትዖት ክፍሉ ደግሞ፡- ዶ/ር ዮሐንስ አድገህ ሰብሳቢ፣ ዶ/ር አበባው ምናዬ ምክትል ሰብሳቢ፣ ዲ/ን ሙሉዓለም ካሣ ጸሐፊ ኾነው በምልዓተ ጉባኤው ተመርጠዋል፡፡

በመጨረሻም በዕለቱ የመርሐ ግብሩ መሪ የነበሩት የEncyclopedia ዝግጅት ክፍል ሰብሳቢው ዶ/ር ዮሐንስ አድገህ ለጉባኤው ተሳታፊዎችና ውይይቱ የተካሔደበትን አዳራሽ በነጻ ለፈቀደው ለሰሜን ሆቴል ምስጋና ካቀረቡና ለእንግዶቹም የምሳ መስተንግዶ ከተደረገ በኋላ መርሐ ግብሩ በጸሎት ተፈጽሟል፡፡

ዘመነ ዕርገት

ሰኔ ፮ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ዕርገት በግእዝ ቋንቋ ማረግ፣ ከታች ወደ ላይ መውጣት ማለት ሲኾን የጌታችን ትንሣኤ በተከበረ በዐርባኛው ቀን የሚውለው ዐቢይ በዓልም ዕርገት ይባላል /ኪዳነ ወልድ ክፍሌ፣ ገጽ ፯፻፷/፡፡

እንደምናስታውሰው ባለፈው ሐሙስ (ሰኔ ፪ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም) ከጌታችን ከመድኀኒታችን ኢየሱስ ዐበይት በዓላት መካከል አንዱ የኾነው በዓለ ዕርገት በቤተ ክርስቲያናችን በድምቀት ተከብሯል፡፡ ከጌታችን የዕርገት በዓል ጀምሮ (ከዐርባኛው ቀን) እስከ ጰራቅሊጦስ ዋዜማ (ዐርባ ዘጠነኛው ቀን) ድረስ ያለው ወቅት ዘመነ ዕርገት ይባላል፡፡

በዓለ ዕርገት ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ከተነሣ በኋላ ለዐርባ ቀናት በግልጽም በስውርም ለቅዱሳን ሐዋርያትና ለቅዱሳት አንስት መጽሐፈ ኪዳንን፣ ትርጓሜ መጻሕፍትን፣ ምሥጢራትን፣ ሕግጋትንና ቀኖናተ ቤተ ክርስቲያንን ሲያስተምር ቆይቶ ወደ ቀደመ ዙፋኑ ወደ ሰማይ ማረጉን የምንዘክርበት ታላቅ የደስታ ቀን ነው፡፡

መጽሐፈ ስንክሳር በዓለ ዕርገት የክብር ባለቤት ጌታችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእኛ በነሣው ሥጋ ከአባቱና ከመንፈስ ቅዱስ ጋራ ወዳለው የአንድነት አኗኗሩ ወደ ሰማይ ያረገበት ዕለት መኾኑን ጠቅሶ፣ በዚህች ቀን ያን ጊዜ በኪሩቤል ላይ ተቀምጦ ወጣ፤ በነፋሳትም ክንፎች ላይ ኹኖ ወጣ /መዝ.፲፯፥፲/ የሚለው የዳዊት ትንቢት መፈጸሙን ያትታል፡፡

በተጨማሪም ሌሊት በራእይ አየሁ፤ እነሆም እንደ ሰው ልጅ የሚመስል በሰማይ ደመና መጣ፤ በዘመናትም ወደ ሸመገለው ደረሰ፡፡ ወደ ፊቱም አቀረቡት፡፡ ወገኖችና አሕዛብ፣ በልዩ ልዩ ቋንቋም የሚናገሩ ኹሉ ይገዙለት ዘንድ ግዛትና ክብር፣ መንግሥትም ተሰጠው፡፡ ግዛቱም የማያልፍ የዘለዓለም ግዛት፤ መንግሥቱም የማይጠፋ ነው፤ /ዳን.፯፥፲፫-፲፬/ የሚለው የነቢዩ ዳንኤል ትንቢት በጌታችን ዕርገት መፈጸሙን ይናገራል /ስንክሳር፣ ግንቦት ፰ ቀን/፡፡

ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅም ዐርባ ስድስተኛውን መዝሙረ ዳዊት በተረጐመበት አንቀጹ ድል መንሳት ባለበት የነጋሪት ድምፅ እግዚአብሔር ዐረገ አለ እንጂ መላእክት አሳረጉት አላለም፡፡ በፊቱ መንገድ የሚመራው አልፈለገም፡፡ በዚያው ጎዳና እርሱ ዐረገ እንጂ፤ በማለት ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአምላካዊ ሥልጣኑ ወደ ሰማይ ማረጉን ተናግሯል፡፡

በተመሳሳይ ምሥጢርም የጌታችንን ዕርገት ከነቢዩ ኤልያስ ዕርገት ጋር በማነጻጸር ነቢዩ ኤልያስ በመላእክት ርዳታ ወደ ሰማይ መወሰዱን /፪ኛነገ.፪፥፩-፲፫/፤ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን የመላእክት ፈጣሪ ነውና በእነርሱ ርዳታ ሳይኾን በገዛ ሥልጣኑ ማረጉን ያስረዳል /ሐዋ.፩፥፱-፲፪/፡፡

ሊቁ በተጨማሪም ሕማም የሚስማማው ግዙፍ ሥጋን ተዋሕዶ ሳለ ከስቅለቱ አስቀድሞ በባሕር ላይ ከሔደ፣ ዛሬ ነፋስን ከፍሎ ሲያርግ ቢታይ ማንም ማን አይጠራጠር፡፡ ሥጋው አልተለወጠምና፤ በማለት ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሞቱና ከትንሣኤው አስቀድሞ በውኀ ላይ እንደተራመደ ኹሉ፣ በለበሰው ሥጋ ወደ ሰማይ ማረግም እንደሚቻለው አስረድቷል /ሃይማኖተ አበው ዘዮሐንስ አፈወርቅ፣ ከፍል ፲፫፣ ምዕ.፷፯፥፲፪-፲፭/፡፡

በበዓለ ዕርገት ሊቃውንቱ ሌሊት በማኅሌት፣ በዝማሬ እግዚአብሔርን ሲያመሰግኑ ያድራሉ፡፡ ሥርዓተ ማኅሌቱ እንዳበቃ የሚሰበከው የነግህ ምስባክም፡- ዘምሩ ለእግዚአብሔር ዘዐርገ ውስተ ሰማይ ሰማይ ዘመንገለ ጽባሕ ናሁ ይሁብ ቃሎ ቃለ ኃይል /መዝ.፷፯፥፴፫/ የሚለው የዳዊት መዝሙር ሲኾን ቀጥተኛ ትርጕሙም በምሥራቅ በኩል ወደ ሰማየ ሰማያት ለወጣ (ላረገ) ለእግዚአብሔር ዘምሩ፤ የኀይል የኾነውን ቃሉን እነሆ ይሰጣል የሚል ኾኖ ምሥጢሩም ነፍሳትን ይዞ ከሲኦል ወደ ገነት ለወጣ፤ አንድም በደብረ ዘይት በኩል ላረገ ለእግዚአብሔር ምስጋና አቅርቡ ማለት ነው፡፡

በተመሳሳይ መልኩ ጌታችን ባረገ በዐሥረኛው ቀን የኀይል ቃል የተባለ መንፈስ ቅዱስን ለሐዋርያት መላኩን፤ እንደዚሁም ይህ ከእናንተ ወደ ሰማይ የወጣው ኢየሱስ ወደ ሰማይ ሲሔድ እንዳያችሁት፣ እንዲሁ ይመጣል፤ ተብሎ እንደ ተጻፈ /ሐዋ.፩፥፲፩/፣ ጌታችን ዳግም እንደሚመጣ፤ እኛም ይህንን የጌታችንን የማዳን ሥራ እያደነቅን ለእርሱ ምስጋና፣ ዝማሬ ማቅረብ እንደሚገባን ያስረዳል፡፡

የነግህ ወንጌል (ከቅዳሴ በፊት የሚነበበው) ደግሞ የሉቃስ ወንጌል ምዕራፍ ፳፬ ቍጥር ፵፭ እስከ መጨረሻው ድረስ ያለው ኃይለ ቃል ሲኾን፣ ኃይለ ቃሉም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሰማየ ሰማያት እንደሚወርድ፣ የሰውን ልጅ ለማዳን ሲል መከራ እንደሚቀበል፣ እንደሚሞት፣ ከሙታን ተለይቶ እንደሚነሣ፣ ወደ ሰማይ እንደሚያርግና ዳግም እንደሚመጣ በነቢያት የተነገረው ትንቢት መፈጸሙንና ለዚህም ቅዱሳን ሐዋርያት ምስክሮች መኾናቸውን ማለትም በመላው ዓለም እየዞሩ ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ የማዳን ሥራ እንደሚሰብኩና በሰማዕትነት እንደሚያልፉ፤ እንደዚሁም ሰማያዊ ሀብትንና ዕውቀትን እስኪያገኙ ድረስ በኢየሩሳሌም እንዲቆዩ መታዘዛቸውን ያስረዳል /ትርጓሜ ወንጌል/፡፡

ይህ ምሥጢር ለጊዜው ሐዋርያትን የሚመለከት ይኹን እንጂ ፍጻሜው ግን ኹላችንም ቅዱሳት መጻሕፍት የተናገሩትን ቃል አብነት አድርገን የእግዚአብሔርን ሰው መኾንና የማዳኑን ሥራ አምነን፣ ሌሎችንም በማሳመን በሃይማኖታችን ጸንተን መኖር እንደሚገባን፤ እግዚአብሔር አምላካችን ኃይሉን፣ ጸጋውን፣ ረድኤቱን እንዲያሳድርብንም ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን መለየት እንደሌለብን የሚያስገነዝብ መልእክት አለው፡፡

በዕለተ ዕርገት በቅዳሴ ጊዜ የሚነበቡ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችም ከቅዱስ ጳውሎስ መልእክት ዕብራውያን ፩፥፩ እስከ ፍጻሜው ድረስ፤ ከሌሎች መልእክታት ደግሞ ፩ኛ ጴጥሮስ ፫፥፲፰-ፍጻሜየሐዋርያት ሥራ ፩፥፩-፲፪ ሲኾኑ፣ ምስባኩም ዐርገ እግዚአብሔር በይባቤ ወእግዚእነ በቃለ ቀርን ዘምሩ ለአምላክነ ዘምሩ የሚለው ኾኖ /መዝ.፵፮፥፭-፮/፣ መልእክቱም በዕልልታና በመለከት ድምፅ ላረገ ለአምላካችን፣ ለጌታችንና ለመድኀኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ምስጋና አቅርቡ ማለት ነው፡፡

ወንጌሉ ደግሞ፣ ማርቆስ ፲፮፥፲፬ እስከ ፍጻሜ ድረስ ሲኾን ቃሉም በነግህ ከተነበበው የወንጌል ክፍል ቃል ተመሳሳይነት አለው፡፡ ቅዳሴውም ቅዳሴ ዲዮስቆሮስ ሲኾን ይኸውም ከሦስቱ አካላት አንዱ የኾነውን የእግዚአብሔር ወልድን (የኢየሱስ ክርስቶስን) ዘለዓለማዊነት የሚያስረዳ፤ ሥጋዌዉን፣ ሕማሙን፣ ሞቱን፣ ትንሣኤዉን፣ ዕርገቱንና ዳግም ምጽአቱንም የሚናገር በመኾኑ በዘመነ ትንሣኤ፣ በዘመነ ዕርገትና በበዓለ ሃምሳ ይቀደሳል፡፡

ቅዱስ ዲዮስቆሮስ በቅዳሴዉ መጀመሪያ ላይ ሀልዎተ እግዚአብሔርንና ምሥጢረ ሥላሴን መሠረት በማድረግ ለእግዚአብሔር ምስጋና ካቀረበ በኋላ፣ ቍጥር ፴፩ ላይ ደግሞ ወበ፵ ዕለት አመ የዐርግ ሰማየ አዘዞሙ እንዘ ይብል ጽንሑ ተስፋሁ ለአብ፤ ከሙታን ተለይቶ በተነሣ በዐርባኛው ቀን በብርሃን፣ በሥልጣን፣ በይባቤ ወደ ሰማይ በሚያርግበት ጊዜ አብ የሚሰድላችሁ መንፈስ ቅዱስን እስክትቀበሉ ድረስ ከዚህ ቆዩ ብሎ አዘዛቸው፤ በማለት መጽሐፍ ቅዱሳዊ በኾነ ቋንቋ የጌታችንን ወደ ሰማይ ማረግና ለሐዋርያት የሰጠውን አምላካዊ ትእዛዝ ይናገራል /ሉቃ.፳፬፥፵፱/፡፡

በዘመነ ዕርገት ውስጥ በሚገኘው እሑድ (ሰንበት) ሌሊት ሊቃውንቱ የሚያደርሱት መዝሙርም በሰንበት ዐርገ ሐመረ የሚል ሲኾን ይኸውም ጌታችን በሰንበት ወደ ታንኳ በመውጣት ባሕርንና ነፋሳትን እንደ ገሠፀ፤ ሐዋርያቱንም ጥርጥር ወደ ልቡናችሁ አይግባ፤ አትጠራጠሩ እንዳላቸው፤ እንደዚሁም ወንጌልን ይሰብኩ፣ ያስተምሩ ዘንድ በመላው ዓለም እንደሚልካቸው፤ በሰማያዊ መንግሥቱ ይኖሩ ዘንድም ዳግመኛ መጥቶ እንደሚወስዳቸው የሚያስገነዝብ መልእክት አለው /ሉቃ.፰፥፳፪-፳፬፤ ዮሐ.፲፬፥፪፤ ፳፥፳፩/፡፡

በቅዳሴ ጊዜ የሚነበቡ ምንባባትም በዕለተ ዕርገት (ሐሙስ) ከተነበቡት ጋር ተቀራራቢነት ያላቸው የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ናቸው፡፡ ለማስታወስ ያህልም ከጳውሎስ መልእክት ሮሜ ፲፥፩ እስከ ፍጻሜው፤ ከሌሎች መልእክታት ፩ኛ ጴጥሮስ ፫፥፲፭ እስከ ፍጻሜው ድረስ ይነበባሉ፡፡ የሐዋርያት ሥራ፣ ምስባኩና ቅዳሴው ከሐሙስ ዕለቱ (ከዕርገት) ጋር አንድ ዓይነት ሲኾን ወንጌሉም ሐሙስ ጠዋት (በነግህ) የተነበበው ሉቃ.፳፥፵፭ እስከ ፍጻሜው ድረስ ያለው ኃይለ ቃል ነው፡፡

በዘመነ ዕርገት ከቅዳሴ በኋላ ከሚቀርቡ ዝማሬያት መካከል ዐርገ ሰማያተ በዐምደ ደመና የሚለው አንደኛው ሲኾን፣ ይህ ዝማሬ ከድንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋ፣ ከነፍሷ ነፍስ የነሣ (የተዋሐደ)፤ ለእስራኤላውያን በሲና በረኀ መና ያወረደ፤ ሶስናን ከረበናት እጅ ያዳነ፤ ሰንበትን ለሰው ልጆች ዕረፍት የሠራ፤ የክርስትና ሃይማኖትን ያቀና (የመሠረተ)፤ ከሰማይ የወረደው የሕይወት እንጀራ፤ በባሕርዩ ምስጋና የሚገባው ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደመና ተጭኖ ወደ ሰማይ ማረጉን የሚያስረዳ ሰፊ ምሥጢር አለው፡፡

በአጠቃላይ በዘመነ ዕርገት በማኅሌት፣ በቅዳሴ፣ በመሥዋዕት ጊዜ በቤተ ክርስቲያን የሚሰጡ ትምህርታት፣ የሚቀርቡ መዝሙራትና የሚነበቡ መጻሕፍት የእግዚአብሔርን ሰው መኾን፣ ተአምራቱን፣ ሕማሙን፣ ሞቱን፣ ነፍሳትን ከሲኦል ማውጣቱን፣ ትንሣኤውን፣ ለሐዋርያትና ለቅዱሳት አንስት መግለጡን፣ በተለይ ደግሞ ዕርገቱን፣ ዳግም ምጽአቱንና ምእመናን በእርሱ አምነው የሚያገኙትን ድኅነት፣ ጸጋና በረከት፣ እንደዚሁም ስለ መንግሥተ ሰማያት የሚያስረዳ ይዘት አላቸው፡፡

ከዚህ በተጨማሪ ምርኮን (የነፍሳትን ወደ ገነት መማረክ) የሚያትቱ ትምህርቶች የሚሰጡትም በዚህ በዘመነ ዕርገት ወቅት ሲኾን፣ ይኸውም በሰይጣን ባርነት ተይዘው የኖሩ ነፍሳት ነጻ የወጡት በኢየሱስ ክርስቶስ አምላካዊ ሥልጣን በመኾኑ ነው፡፡ ምርኮን ማረከህ፤ ወደ ሰማይም ወጣህ፡፡ ስጦታህንም ለሰዎች ሰጠህ፡፡ ያድሩ ዘንድ ይክዱ ነበርና እንዳለ ቅዱስ ዳዊት /መዝ.፷፯፥፲፰/፡፡ ይህም ጌታችን ነፍሳትን ይዞ ከሲኦል ወደ ገነት መውጣቱንና ለምእመናን የሥላሴ ልጅነትን እንደሰጠ የሚያስረዳ ሲኾን፣ ያድሩ ዘንድ ይክዱ ነበር ሲልም በክህደት ይኖሩ የነበሩ ኹሉ ጌታችን በሰጠው ልጅነት ተጠርተው፣ አምነውና በሃይማኖት ጸንተው መኖራቸውን ሲያመለክት ነው፡፡

ከላይ እንደ ተመለከትነው ዘመነ ዕርገት ወደ ላይ የመውጣት፣ የማረግ፣ ከፍ ከፍ የማለትና የማደግ ወቅት ነው፡፡ እኛም በሞት ከመወሰዳችን በፊት ለመንግሥቱ የሚያበቃ ሥራ ያስፈልገናልና ሕሊናችን በጽድቅ ሥራ እንዲያርግ (ከፍ ከፍ እንዲል) ዘወትር በጾም፣ በጸሎት መትጋት ይኖርብናል፡፡ ምክንያቱም ዕርገት ሲባል በአካል ማረግን ወይም ወደ ሰማይ መውጣትን ብቻ ሳይኾን፣ በአስተሳሰብና በምግባር መለወጥን፣ በአእምሮ መጎልመስንም ያመለክታልና፡፡

በሞቱ ሕይወታችንን ለመለሰልን፤ በትንሣኤው ትንሣኤያችንን፣ በዕርገቱ ክብራችንን ለገለጠልን ለጌታችን ለመድኀኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ለዘለዓለሙ ክብር ምስጋና ይደረሰው፡፡ ዜና ብሥራቱን፣ ፅንሰቱን፣ ልደቱን፣ ዕድገቱን፣ ስደቱን፣ ተአምራቱን፣ ሕማሙን፣ ሞቱንና ትንሣኤውን በሰማንበት ዕዝነ ልቡናችን፣ ባየንበት ዓይነ ሕሊናችን ዕርገቱንም እንድንሰማና እንድናይ ዕድሜ ለንስሐ ሰጥቶ እስከ ዛሬ ድረስ እንደ ጠበቀን ኹሉ፣ ዳግም ለፍርድ በሚመጣበት ጊዜም እናንተ ቡሩካን ወደ እኔ ኑ የሚለውን የሕይወት ቃል እንዲያሰማን ቅዱስ ፈቃዱ ይኹንልን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፡-

መጽሐፍ ቅዱስ፣ የኢትዮጵያ መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር፤ አዲስ አበባ፣ ፳፻ ዓ.ም፡፡

መዝሙረ ዳዊት ንባቡና ትርጓሜው፣ ተስፋ ገብረ ሥላሴ፤ አዲስ አበባ፣ ፲፱፻፹፪ ዓ.ም፡፡

ማኅቶተ ዘመን፣ መ/ር በሙሉ አስፋው፣ ገጽ ፻፺፩-፻፺፬፤ አዲስ አበባ፣ ፳፻፩ ዓ.ም፡፡

ዝማሬ ወመዋሥዕት፣ ትንሣኤ ማሳተሚያ ድርጅት፤ አዲስ አበባ፣ ፲፱፻፹፱ ዓ.ም፡፡

ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ

ሰኔ ፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈሰ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን::

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ መደበኛ ስብሰባ በዓመት ሁለት ጊዜያት እንዲሆን በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ ፭ ቍጥር ፻፷፬ በተደነገገው መሠረት ምልዓተ ጉባኤው የዘንድሮዉን መደበኛ የርክበ ካህናት ስብሰባ የጉባኤው መክፈቻ ሥርዓተ ጸሎት ከተፈጸመበት ከበዓሉ ዋዜማ ከግንቦት ፲፮ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ጀምሮ እስከ ሰኔ ፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ድረ ለዐሥራ ስድስት ቀናት ያህል ባደረገው ጉባኤ ጠቀሜታ ባላቸው የአጀንዳ ነጥቦች ተወያይቶ ውሳኔዎችን አሳልፏል፡፡

ከእነዚህ መካከል የሚከተሉት በዋናነት ይጠቀሳሉ፤

፩. የ፳፻፰ ዓ.ም የርክበ ካህናት ጉባኤን በተመለከተ ቅዱስ ፓትርያርኩ ያደረጉት የመክፈቻ ንግግር እንዳበቃ ጉባኤው ሥራውን ቀጥሏል፡፡

፪. የቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት ዓመታዊ ሪፖርት በጽሑፍ ቀርቦ ጉባኤው ካዳመጠ በኋላ በሪፖርቱ ላይ ውይይት በማድረግ ለወደፊቱ የሚወሰኑት ኹሉ የአፈጻጸምƒƒ‚ ችግር እንዳይደርስባቸው ክትትል ይደረግ ዘንድ ተወስኗል፡፡

፫. እስከ አሁን እየተሠራበት ያለው ቃለ ዓዋዲ የቤተ ክርስቲያናችን መተዳደሪያ ደንብ ወቅቱን ባገናዘበ መልኩ እንዲሻሻል በተሰጠው መመሪያ መሠረት የተዘጋጀው ረቂቅ ቀርቦ ምልዓተ ጉባኤው ከተነጋገረበትና ከታየ በኋላ የረቂቁ ዝግጅት በቋሚ ሲኖዶስ ታይቶ እንዲታተም ተወስኗል፡፡

፬. ስለ ቅዱስ ፓትርያርክ እንደራሴ አስፈላጊነት ጉዳይ ቅዱስ ሲኖዶስ ከተነጋገረ በኋላ የእንደራሴ አስፈላጊነት በምን ዓይነት ሕግ ላይ ተመሥርቶ መመረጥ አለበት የሚለዉን በማጥናት ለጥቅምቱ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የሚያቀርቡ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትን ጨምሮ ሰባት አባላት እንዲመረጡ ተደርጓል፡፡

፭. ተፈጥሮ ባስከተለው ድርቅ ምክንያት በየመጠለያው ለሚገኙ ወገኖች የዕለት ደራሽ ርዳታ፣ ለተፈናቀሉ ወገኖችም ለመልሶ ማቋቋሚያ አገልግሎት የሚውል የገንዘብና የቁሳቁስ ርዳታ ይደረግ ዘንድ ቤተ ክርስቲያን ጥሪዋን ታስተላልፋለች፤ የድርሻዋንም አስተዋፅኦ አድርጋለች፡፡

፮. በቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ገዳማት የሚያገለግል ሕንፃ ƒƒመገንባት ይቻ ዘንድ ቦታ እንዲሰጥ ከገዳሙ ማኅበረ መነኰሳት የቀረበውን ጥያቄ ምልዓተ ጉባኤው የተቀበለው ስለኾነ፣ በቤተ ክርስቲኒቱ ማእከላዊ አስተዳደር በኩል ቦታ ተፈልጎ እንዲሰጥ ተዋስኗል፡፡

፯. ቅዱስ ሲኖዶስ በየአህጉረ ስብከቱ ክፍት በኾኑ መንበረ ጵጵስናዎች ብቁ የኾኑ ኤጲስ ቆጶሳትን መርጦ ለመሾም ባለው ዕቀድ መሠረት፣

ፈተናዉንና መሰናክሉን ኹሉ አልፈው ዕውቅና ያገኙትን፤

በብሔር ዓቀፍና በዓለም ዓቀፍ ትምህርት የበሰሉትን፤

የወቀውቱንም ችግር ይፈታሉ ተብለው እምነት የተጣለባቸውንና የሚጣልባቸውን፤

ለተልእኮ የሚፋጠኑትን መነኰሳት በመመርመር፣ በማጥናትና በማጣራት ውጤቱን እስከ ሰኔ ፴ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ድረስ የሚያቀርብ አስመራጭ ኰሚቴ እንዲቋቋም ተደርጓል፡፡

፰. ሀ. ብፁዕ አባ ያሬድ ሊቀ ጳጳስ የኢትዮጵያ ሱማሌ ሀገረ ስብከት ሥራን እንደያዙ በአርሲ ሀገረ ስብከት፤

ለ.ብፁዕ አባ እንጦንስ ሊቀ ጳጳስ በምዕራብ ሐረርጌ ሀገረ ስብከ፤

ሐ.ብፁዕ አባ ያዕቆብ ሊቀ ጳጳስ በደቡብና ምዕራብ አፍሪካ አህጉረ ስብከት፤

መ.ብፁዕ አባ እንድርያስ ሊቀ ጳጳስ የሊቃውንት ጉባኤ የበላይ ሓላፊነቱን ሥራ እንደያዙ በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል የበላይ ሓላፊ በመኾን ተመድበው እንዲሠሩ ምልዓተ ጉባኤው ተስማምቷል፡፡

፱. በውጭ ላሉት አህጉረ ስብከት ጥናት ተደርጎ በቋሚነት የሚሠሩ አባቶች እስኪመደቡ ድረስ፣

ሀ/ ሰሜን፣ ሰሜን ምሥራቅና ሰሜን ምዕራብ አውሮፓ አህጉረ ስብከት፣

ለጊዜው በብፁዕ አባ ሙሴ የደቡብ ምዕራብና የደቡብ ምሥራቅ አውሮፓ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ተደርቦ እንዲሠራ፤

ለ/ አውስትራልያ ሀገረ ስብከት፣

በብፁዕ አባ ሔኖክ የምዕራብ ወለጋና የአሶሳ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ተደርቦ እንዲሠራ፤

ሐ/ ምሥራቅ አፍሪካ፣ ኬንያና ጅቡቲ አህጉረ ስብከት፣

በብፁዕ አባ ዳንኤል የድሬዳዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ተደርቦ እንዲሠራ፤

መ/ ሥራቅ አፍሪካ፣ ሰሜን ሱዳንና ግብፅ አህጉረ ስብከት፣

በብፁዕ አባ ሉቃስ በክልል ትግራይ ዞን ወልቃይት ጸገዴ ሰቲት ሑመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ተደርቦ እንዲሠራ ኾኖ፣

በተጨማሪም የትንሣኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ቤት የበላይ ሓላፊ ኾነው እንዲሠሩ፤

ሠ/ ደቡብ ሱዳን ሀገረ ስብከት፤

በብፁዕ አባ እስጢፋኖስ የጅማ፣ የኢሉባቡርና ጋምቤላ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ተደርቦ እንዲሠራ ሲል ምልዓተ ጉባኤው በአንድ ድምፅ ተስማምቶ ወስኗል፡፡

፲. በውጭ አህጉረ ስብከት ካሉት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ጋር ያለው የሰላሙ ንግግር ይቀጥል ዘንድ ሰላም ለማንኛውም መሠረት መኾኑ ታምኖበት ይህንኑ ሰላም ለማምጣት አስፈላጊው ጥረት ኹሉ እንዲደረግ፡፡

፲፩. ስለ አዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ረዳት ሊቀ ጳጳስ ምደባ ጉዳይ ቅዱስ ሲኖዶስ ከተወያየ በኋላ በሕገ ቤተ ክርስቲያን አንቀጽ ፶ መሠረት ብፁዕ አባ ሕዝቅኤል በያዙት ሀገረ ስብከት ሥራቸው ላይ ደርበው እስከ ጥቅምት ወር ፳፻፱ ዓ.ም ድረስ የፓትርያርክ ረዳት ሊቀ ጳጳስ ኾነው እንዲሠሩ ተስማምቷል፡፡

፲፪. በየሦስት ዓመቱ የሚደረገው የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ እኪኪያጅና የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ምርጫ ካሉት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት መካከል በማወዳደር፡-

ሀ. ብፁዕ አባ ዲዮስቆሮስ ሊቀ ጳጳስ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣

ለ. ብፁዕ አባ ሳዊሮስ ሊቀ ጳጳስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ኾነው ለሚቀጥሉት ሦስት ዓመታት እንዲሠሩ በቅዱስ ሲኖዶስ ተመርጠዋል፡፡

፲፫. በሕፃናትና ቤተሰብ ጉዳይ ድርጅት ሓላፊነት በቤተ ክርስቲያናችን እየተረዱ የሚያድጉ እጓለ ማውታ ሕፃናት በየአህጉረ ስብከቱ መኖራቸው የሚታወቅ ነው፤ ይኸው የሕፃናትና የቤተሰብ ጉዳይ ድርጅት እጓለ ማውታ ሕፃናትን በማሳደግና በማስተማር ረገድ ለሀገራችንና ለቤተ ክርስቲያናችን ትልቅ አለኝታ ስለኾነ፣ አስከ አሁን ከነበረው ይዘት በበለጠ ተጠናክሮ እንዲቀጥል በቅዱስ ሲኖዶስ ተወስኗል፡፡

፲፬. የቤተ ክርስቲያናችን እምነትና ሥርዓተ አምልኮ እስከ አሁን ድረስ ተከብሮና ተጠብቆ እንደ ኖረ ኹሉ አሁንም ከመንበረ ፓትርያርክ እስከ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ያለው የመንፈሳዊና የማኅበራዊ አገልግሎት መዋቅር በበለጠ ተጠናክሮ ይቀጥል ዘንድ መመሪያ ተሰጥቷል፡፡

፲፭. በቤተ ክርስቲያኒቱ ማእከላዊ አሰዝተዳደር ቀልጣፋና ቅንነት የሰፈነበት አሠራር እንዲኖር፣ በየደረጃው የተዘረጉትም የልማት አውታሮች የበለጠ ውጤት እንዲኖራቸው ለማስቻል፣ ከመንበረ ፓትርያርክ ሥራ አስኪያጅ ጀምሮ ኹሎችም የየአህጉረ ስብከቱ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ ሓላፊነት ያለባቸው ስለኾነ ተከታትለው እየሠሩ እንዲያሠሩ ተወስኗል፡፡

፲፮. በመከናወን ላይ ለሚገኘው የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ፕሮጀክት አጀማመር ኹሉም ኅብረተሰብ እጁን ሲዘረጋ እንደቆየ ኹሉ፣ አሁንም ለፕሮጀክቱ አፈጻጸም መላው ኀብረተሰብ የበኩሉን ድርሻ ይፈጽም ዘንድ ቀዱስ ሲኖዶስ ያሳስባል፡፡

፲፯. ከሀገራችን ኢትዮጵያ ውጭ ባሉት አንዳንድ አህጉር እየደረሰ ያለውን የተፈጥሮና ሰው ሠራሽ ችግር በጆራችን እንሰማለን፤ በዓይናችንም እናያለን፡፡ ለማስረጃም ያህል፡-

በመሬት መንቀጠቀጥ፣ በጎርፍ መጥለቅለቅና በሰደድ እሳት ዘግናኝ አደጋ የሚደርስ ኅልፈተ ሕይወት፤

በእርስበርስ የውስጥ ጦርነት የደረሰውና እየደረሰ ያለው ዕልቂት፤

የእግዚአብሔርን ህልውና በሚፈታተኑ አንዳንድ ግለሰቦች ግንዛቤ ጉድለት እየደረሰ ያለው የጦርነት አደጋ፤

በየብስ፣ በውቅያኖሶችና በሰማይ ላይ በሚበሩ አውሮፕላኖች የሚደርሰው ዘግናኝ ዕልቂትና የመሳሰሉት ከሚጠቀሱት መካከል ናቸው፡፡

ስለዚህ እግዚአብሔር አምላካችን ጉዳት ለደረሰባቸው መጽናናትን፣ መረጋጋትን እንዲሰጥልን፤ ቅን ልቡና፣ ትሑት ሰብእና ለሚጎድልባቸው የኅብረተሰብ ክፍሎችም ትዕግሥቱን፣ ርኅራኄውን እንዲያበዛልን እንጸልያለን፡፡

በመጨረሻም በሀገራችን ጎልቶ የሚታየው ድህነት እንዲወገድ፤ የተራበው፣ የተጠማው፣ የታረዘው መሠረታዊ ፍላጎቱ ተሟልቶለት እንዲኖር፤ በሀገራችን ኢተዮጵያ፣ በዓለሙም ኹሉ ሰላም እንዲሰፍን ቅዱስ ሲኖዶስ በመጸለይ ስብሰባውን በጸሎት አጠናቋል፡፡

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ፤ ይቀድስ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፤

አሜን!

አባ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ

ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም

ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

ሰኔ ፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም፡፡

፲፰ኛው የአሜሪካ ማእከል ጠቅላላ ጉባኤ ተካሔደ።

ግንቦት ፳፭ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በአሜሪካ ማእከል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ትቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የአሜሪካ ማእከል ፲፰ኛ ጠቅላላ ጉባኤ በሲያትል ዋሺንግተን ቅዳሜ ግንቦት ፳ እና እሑድ ግንቦት ፳፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ተካሔደ።

በጉባኤው ወደ ፬፻ የሚደርሱ የማእከሉ አባላት፤ የዲሲና የአካባቢው እንዲሁም የካሊፎርንያና ምዕራብ አሜሪካ አህጉረ ስብከት ተወካዮችና የሥራ አስፈጻሚ አባላት፤ የአብያተ ክርስቲያናት አስተዳዳሪዎችና ካህናት፣ የሰንበት ትምህርት ቤት አባላትና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።

ጉባኤው በጸሎተ ኪዳን በተጀመረበት ቅዳሜ ግንቦት ፳ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም የማእከሉ ሰብሳቢ ዶ/ር ሕልምነህ ስንሻው የእንኳን ደኅና መጣችሁና የመክፈቻ ንግግር ካደረጉ በኋላ በማእከሉ የተተገበሩ ዋና ዋና የአገልግሎት ሥራዎችን ዘገባ አቅርበዋል። የዲሲ እና የአካባቢው ሀገረ ስብከት ዋና ጸሐፊ መልአከ ሰላም ቀሲስ ዶ/ር መሥፍን ተገኝም የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ የብፁዕ አቡነ ፋኑኤልን መልእክት ለጉባኤው ካስተላለፉ በኋላ በመልአከ ሰላም ቀሲስ ደጀኔ ሽፈራው “ሥራ የበዛበት ትልቅ በር” /፩ኛቆሮ. ፱፥፲፮/ በሚል ኃይለ ቃል ትምህርተ ወንጌል ተሰጥቷል፡፡

በመቀጠል የማእከሉ የአገልግሎት ክፍሎች ዓመታዊ ጠቅላላ ሪፖርትና የቀጣይ ዓመት ዕድቅ ለጉባኤው ቀርቧል፡፡ በቀረበው ሪፖርትም በንዑሳን ማእከላት በርካታ ትምህርታዊ ጉባኤዎች እንደተካሔዱ፣ በልዩ ልዩ ከተሞች የማኅበረሰብ ቴሌቪዥን ፕሮግራም እንደተጀመረ፣ ለገዳማት እና አብነት ትምህርት ቤቶች፣ እንዲሁም ኢአማንያንን ለማስተማርና ለማስጠመቅ ለተዘረጋው የስብከተ ወንጌል ፕሮጀክት ከአባላት እና ከምእመናን የተሰበሰበ የእርዳታ ገንዘብ ወደ ዋናው ማእከል እንደተላከ ተገልጿል።

የማኅበረ ቅዱሳን ዋናው ማእከል ተወካይ ሊቀ ትጉሃን ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ሥዩም የዋናውን ማእከል መልእክት እና ሪፖርት ባቀረቡበት ወቅት ከጉባኤው ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ምላሽ ከመስጠታቸው በተጨማሪ የተሐድሶ መናፍቃንን እንቅስቃሴና ወቅታዊ ጉዳዮችን በማስመልከት ሰፊ ማብራሪያ አቅርበዋል።

በሁለቱ ቀናት ጉባኤ ላይ በሲያትል ንዑስ ማእከል የአቡነ ጎርጎርዮስ ትምህርት ቤቶች ተማሪዎች ውዳሴ ማርያምና ሰዓታት በንባብና በዜማ፤ የጸሎተ ቅዳሴ ተሰጥኦና ምስባክ፤ እንደዚሁም የአብነት ትምህርትን አሰጣጥና ሒደት የሚያሳይ ሥርዓተ ማኅሌት፣ ቅኔ፣ የመጻሕፍት ትርጓሜ እና የተለያዩ መንፈሳዊ ዝግጅቶችን አቅርበዋል።

በተጨማሪም የሲያትል ንዑስ ማእከል የአገልግሎት ተሞክሮዉን ለጉባኤው ያካፈለ ሲኾን፣ የማእከሉ የአገልግሎት ክፍሎች የበጀት ሪፖርትም ለጉባኤው ቀርቦ ውይይት ተደርጎበታል። ከስድስት ወር በኋላ የማእከሉ የዕቅድ ክለሳ እንደሚደረግም በጉባኤው ተገልጿል።

እንዲሁም ዝክረ አበው በሚል መርሐ ግብር የሊቀ ጉባኤ አባ አበራ ሰባተኛ ዓመት የዕረፍት መታሰቢያ በማስመልከት የተዘጋጀ ፊልም ለእይታ በቅቷል።

በዕለቱ ላለፉት ሁለት ዓመታት ማዕከሉን ይመራ የነበረው የሥራ አስፈጻሚ የሥራ ዘመን በመፈጸሙ፣ ለሚቀጥሉት ሁለት ዓመታት ማእከሉን በሥራ አስፈጻሚነት የሚመሩ ፲፫ አባላት በጸሎትና በዕጣ ተመርጠዋል።

በጉባኤው ማጠቃለያ በማእከሉ ፲፰ኛ ጠቅላላ ጉባኤ አዘጋጅ ኮሚቴ የዝግጅቱ ሒደትና በሲያትል ከተማ የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት የሰበካ ጉባኤ አባላት፣ የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶችና ምእመናን በልዩ ልዩ መንገድ ያበረከቱት ከፍተኛ አገልግሎት በዝርዝር የቀረበ ሲኾን ይህ አሳታፊነትና ከአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ጋር በቅንጅት የመሥራት ልምድ ለሌሎች ንዑሳን ማእከላትና ግንኙነት ጣቢያዎች ያለው አርአያነት የጎላ መኾኑ ተገልጿል።

በመጨረሻም ፲፱ኛው የማእከሉ ጠቅላላ ጉባኤ በቦስተን፣ ፳ኛው ጠቅላላ ጉባኤ ደግሞ በቨርጂንያ እንዲካሔድ ተወስኖ ጠቅላላ ጉባኤው በዝማሬ እና በጸሎት ተጠናቋል።

የቅዱስ ያሬድን ፲፭፻፫ኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ የቅኔ ውድድር ተካሔደ፡፡

ግንቦት ፳፭ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በጎንደር ማእከል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ት/ቤተፐች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን በጎንደር ማእከል አዘጋጅነት ግንቦት ፲፬ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም የቅዱስ ያሬድን ፲፭፻፫ኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ በጎንደር ከተማ በርእሰ አድባራት ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን የቅኔ ውድድር ተካሔደ፡፡

የውድድሩ ተሳታፊ ጉባኤ ቤቶች፡- የደብረ ፀሐይ ቍስቋም ማርያም፣ የደብረ ምሕረት አቡን ቤት ቅዱስ ገብርኤል፣ የቀዳሜ አድባራት አበራ ጊዮርጊስ፣ የመካነ ሕይወት ፊት አቦ እና የደብረ ገነት አዘዞ ቅዱስ ሚካኤል ቅኔ ጉባኤ ቤቶች ሲኾኑ፣ መምህራኑ የመረጧቸው ደቀ መዛሙርትም ጉባኤ ቤቶቹን ወክለው ለውድድር ቀርበዋል፡፡

ውድድሩን በዳኝነት የመሩትም መምህር ፍቅረ ማርያም የመንበረ መንግሥት መድኃኔ ዓለም የ፬ቱ ጉባኤያት ምክትል መምህር፣ ሊቀ ብርሃናት ኤልያስ አድማሴ በዐቢየ እግዚእ ኪዳነ ምሕረት የብሉይ ኪዳን መምህር እና መምህር ቃለ ሕይወት በመካነ ነገሥት ግምጃ ቤት የሐዲስ ኪዳን መምህር ሲኾኑ የውድድሩ መሥፈርቶችም አንደኛ የቅኔው ምሥጢር፣ ሁለተኛ የዜማው ልክ፣ ሦስተኛ ገቢር ተገብሮ አገባብ፣ አራተኛ የቃላት አመራረጥ እና አምስተኛ የጊዜ አጠቃቀም ናቸው፡፡ እያንዳንዱ መሥፈርት ፳፣ ባጠቃላይም ፻ ነጥቦችን የያዘ ሲኾን ለእያንዳንዱ ተወዳዳሪም የ፲፭ ደቂቃ የማቅረቢያ ጊዜ ተሰጥቶታል፡፡

በውድድሩ ከአንደኛ አስከ ሦስተኛ ደረጃ የያዙት የወንጌል አንድምታ ትርጓሜ መጻሕፍትን፤ አራተኛና አምስተኛ የወጡት ደግሞ የትንቢተ ኢሳይያስን አንድምታ ትርጓሜ መጽሐፍ ተሸልመዋል፡፡ ይኸውም ቅኔ ተምረናል በቃን ብለው እንዳያቆሙ እና ቀጣይ መጻሕፍትን እንዲማሩ ለማሳሰብ ነው፡፡

በመርሐ ግብሩ ላይ የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የማእከሉ ሰብሳቢ መምህር ዓለማየሁ ይደግ እንደተናገሩት የውድድር መርሐ ግብሩ የተዘጋጀበት ዓላማ በጉባኤ ቤቶች መካከል መልካም የሆነ የውድድር መንፈስ እንዲኖር፣ ተማሪዎቹ ራሳቸውን እንዲፈትሹ ለማድረግ፣ የቅኔ ትምህርት በማኅበረሰቡ ዘንድ እንዲታወቅ፣ የበታቾቻቸውን ለማነሣሣት እና በዋናነት ቅዱስ ያሬድን ለመዘከር ነው፡፡

የጎንደር ከተማ ወረዳ ቤተ ክህነት ሊቀ ካህናት ሊቀ አእላፍ ጥበበ አወቀ በመርሐ ግብሩ ላይ ተገኝተው እንደዚህ ዓይነቱ መርሐ ግብር እየቀዘቀዘ የመጣውን የአብነት ትምህርት በተለይ የቅኔ ትምህርት እንደሚያጠናክር ጠቅሰው ይህም ማኅበረ ቅዱሳንን እንደሚያስመሰግነው ገልጸዋል፡፡ አያይዘውም ለደቀ መዛሙርቱ አባቶቻችን ይህን ትምህርት በእግዚአብሔር ኃይል ጸንተው፣ ኮቸሮ በልተው፣ በውሻ ተበልተው አቆይተውናል፤ እኛም ጠብቀን ለትውልድ ማቆየት ይኖርብናል ሲሉ ተናግረዋል፡፡

በመርሐ ግብሩ ላይ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ በስድስቱም ጉባኤ ቤቶች የሚገኙ በርካታ የአብነት ተማሪዎች እና በርካታ ምእመናን የተገኙ ሲኾን፣ ከምእመናኑም ይህ የቅኔ ትምህርት እንዲስፋፋ ሰፊ ትኩረት ተሰጥቶት ሊሠራ እንደሚገባው አስተያየት ተሰጥቷል፡፡

የጎንደር ማእከል መዘምራንም ቅዱስ ያሬድን የሚዘክሩ የሰማይ ምስጋና የሚል የንስሐ መዝሙር እና ያሬድ ማኅሌታይ ለእግዚአብሔር ካህኑ የሚል ወረብ አቅርበዋል፡፡

የመርሐ ግብሩ መምህር በጽሐ ዓለሙ በመንበረ መንግሥት መድኃኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን የ፬ቱ ጉባኤያት ምክትል መምህር በአብነት ትምህርት ቤት ሦስት ዓይነት ተማሪ አለ፤ እነሱም፡- እግረ ተማሪ፣ ልብሰ ተማሪ እና ልበ ተማሪ ናቸው ካሉ በኋላ ኹላችንም ልበ ተማሪን ኾነን ትምህርታችንን በሚገባ መማር አለብን ብለዋል፡፡

በመጨረሻም በአባቶች ጸሎት መርሐ ግብሩ ተጠናቋል፡፡ ይህ መርሐ ግብር በፋና ኤፍ ኤም 98.1 የሬድዮ ጣቢያም የሚዲያ ሽፋን ማግኘቱ የሚታወስ ነው፡፡

የአዳማ ማእከል የሕክምና አገልግሎት ሰጠ፡፡

ግንቦት ፳፭ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በአዳማ ማእከል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የአዳማ ማእከል የቅዱሳት መካናት ልማት እና ማኅበራዊ አገልግሎት ክፍል በዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም ለሚገኙ አባቶችና እናቶች መነኮሳት እንዲሁም ለአብነት ተማሪዎች ግንቦት ፯ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም የሕክምና አገልግሎት ሰጠ፡፡

በሕክምና አገልግሎቱም በአዳማ ማእከል፣ በደብረ ዘይት ወረዳ ማእከልና በአዱላላ ግንኙነት ጣቢያ የሚገኙ ስፔሻሊስት ሐኪሞች፣ ሜዲካል ዶክተሮች፣ የጤና መኮንኖች፣ የላቦራቶሪ ቴክኒሻኖች እና የአዳማ ሆስፒታል ሜዲካል ኮሌጅ ግቢ ጉባኤ የሕክምና ተማሪዎች በአጠቃላይ ፴፰ የሕክምና ባለሞያዎች ተሳትፈዋል፡፡

በሕክምና አገልግሎቱም ለገዳሙ መነኮሳት እና አብነት ተማሪዎች ሙሉ የጤና ምርመራና የመድኃኒት ድጋፍም ተደርጓል፡፡ ለአባቶች መነኮሳትና ለእናቶች መነኮሳይያት የስኳር፣ የደም ግፊት እና የዓይን ምርመራ ተደርጎላቸዋል፡፡ የመድኃኒት አቅርቦቱም ከዋናው ማእከል ቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል እና ከአንድ በጎ አድራጊ ወንድም የተገኘ ነው፡፡ የአዳማ ኢዮር ክሊኒክ የመድኃኒትና የሕክምና መመርመሪያ መሣሪያ ከማቅረቡ ባሻገር የክሊኒኩ ስፔሻሊስት ሐኪሞችም ከፍተኛ አገልግሎት ፈጽመዋል፡፡

በዕለቱ ሕክምና የተደረገላቸው አባቶች መነኮሳት፣ እናቶች መነኮሳይያትና የአብነት ተማሪዎች ከ፪፻፶ የሚበልጡ ሲኾን፣ ከሕክምናው በተጨማሪ ለአብነት ተማሪዎች የግልና የአካባቢን ጤና አጠባበቅ የተመለከተ ሥልጠና በጤና ባለሞያዎች ተሰጥቷቸዋል፡፡ ከዚህ ጋር ተያይዞ በአዳማ ማእከል የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ክፍል ለአብነት ተማሪዎች የተዘጋጀው አልባሳት፣ የገላና የልብስ ሳሙና በገዳሙ በኩል ለአብነት ተማሪዎቹ እንዲከፋፈል ተደርጓል፡፡

የገዳሙ አባቶች፣ እናቶች መነኮሳትና እና የአብነት ተማሪዎቹ በተደረገላቸው የሕክምና፣ የአልባሳት እና የጤና መጠበቂያ ድጋፍ እጅግ መደሰታቸውን ገልጸው ማኅበረ ቅዱሳን በገዳማት ላይ እየሠራ ያለው አገልግሎት የሚያስመሰግነው መኾኑንና ይህንንም ሁልጊዜ ሲያስታውሱት እንደሚኖሩ በመጥቀስ ማኅበሩ በገዳማት ላይ የሚያደርገውን አገልግሎት አጠናክሮ እንዲቀጥል በማሳሰብ ማኅበሩን ያስፋልን ይጠብቅልን በማለት መርቀው የሕክምና ቡድኑን በቡራኬና በጸሎት አሰናብተዋል፡፡

አምስተኛው ዐውደ ርእይ በሰላም ተጠናቀቀ፡፡

ግንቦት ፳፫ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ማኅበረ ቅዱሳን የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርቲያንን አስተምህሮዋን እንጠንቅቅ፤ ድርሻችንን እንወቅ በሚል መሪ ቃል ከግንቦት ፲፯-፳፪ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ለስድስት ቀናት በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል ያዘጋጀው አምስተኛው ዐውደ ርእይ ግንቦት ፳፪ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ከምሽቱ 4፡00 በሰላም ተጠናቀቀ፡፡

ዐውደ ርእዩ ከተጀመረበት ዕለት እስከ ተጠናቀቀበት ሰዓት ድረስ በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ በብዙ ሺሕ ምእመናን፣ በመንግሥት ባለ ሥልጣናትና በሌሎች ቤተ እምነት ተከታዮችም ተጎብኝቷል፡፡

በዐውደ ርእዩ ከተሳተፉ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት መካከል ብፁዕ አቡነ ሉቃስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የሰቲት ሑመራ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ይህ ዛሬ ያየነው በማኅበረ ቅዱሳን የተዘጋጀ ትልቅና አስደናቂ ዐውደ ርእይ ነባሩን ኢትዮጵያዊ ሥርዓት፣ ቅርስ፣ ታሪክና ትውፊት የሚገልጽ ዐውደ ርእይ ነው፤ በመኾኑም በጣም የሚወደድ፣ የሚከበርና የሚደነቅ ነው ብለዋል፡፡ አክለውም ይህንን ነባር ሥርዓት ለማጥፋት የሚጥሩ ብዙ ሐሳውያንን ስላሉ ኹላችንም ከመንበረ ፓትርያርክ ጀምሮ እስከ አጥቢያ ድረስ ጠንክረን መሥራት ይኖርብናል፤ ዐውደ ርእዩም እስከ ወረዳ ድረስ መታየት ይገባዋል ካሉ በኋላ በርቱ፤ ጠንክሩ፡፡ ኹሉም ነገር ለሰላም፣ ድህነትን ለማጥፋት፣ አንድነትን ለማጽናት፣ በአጠቃላይ ድንቁርናን ለማስወገድ መኾን ይኖርበታል በማለት አባታዊ ምክራቸውን አስተላልፈዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ኤልያስ የጋሞ ጎፋና የደቡብ ኦሞ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የሲኖዶስ አባል ደግሞ ይህንን የመሰለ ያማረ ጉባኤ ሳይ በጆሯችን የሰማነውን በዓይኖቻችንም ያየነውን እንመሰክራለን ተብሎ እንደተጻፈ የሰማሁትንና ያየሁትን መመስከር ግድ ይለኛል፡፡ ልጆቻችንን በዚህ ደረጃ ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል ያበቋቸው ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ናቸው፡፡ ብፁዕነታቸው እኔ ለኩሸዋለሁ፤ እናንተ አንድዱት የሚል ቃል ተናግረው ነበር፡፡ በእውነትም እርሳቸው የለኮሱት መንፈሳዊ ሕይወት፣ መንፈሳዊ አገልግሎት ነዷል፡፡ ከኢትዮጵያም ተርፎ በመላው ዓለም ተዳርሷልና ይህንን በማየታችን እጅግ በጣም ደስ ብሎናል ሲሉ የተሰማቸውን ደስታ ገልጸዋል፡፡ በተጨማሪም እግዚአብሔር የሚቋረጥ ሥራ አይወድምና በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የአባቶቻቸውን አደራ እንደ ጠበቁ ልጆች ማኅበረ ቅዱሳንም የአባታችሁን የብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስን አደራ በመጠበቅ አገልግሎታችሁን ልትቀጥሉ፤ ፈተናዎችንም በመወያየትና በመነጋገር ልታልፏቸው ይገባል የሚል አባታዊ ምክር ለግሰዋል፡፡

በሰሜን አሜሪካ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል የኾኑት ብፁዕ አቡነ ፋኑኤልም የዚህ ታላቅ ማዕድ ተካፋይ በመኾኔ እጅግ በጣም ደስ ብሎኛል፡፡ በእናንተ በልጆቻችንም መንፈሳዊ ኩራት ይሰማናል፡፡ ልበ አምላክ ዳዊት በአባቶች ፈንታ ልጆች ተወለዱልሽ እንዳለው ኹሉ ተዋሕዶ እምነታችን እንደዚህ ለሃይማኖታችሁ የምትቆረቆሩ የምታስቡ ልጆች በማግኘቷና እኛም እንደዚህ ዓይነት ትውልድ ባለበት ሰዓት በመነሣታችን እጅግ ደስ ይለናል ሲሉ ስሜታቸውን ከገለጹ በኋላ ማኅበሩ የሠራው ሥራ የሚያስመሰግነው ቢኾንም በቅዱስ ወንጌል እንደ ተጻፈው እኛ ለጌታ የማንጠቅም ባሪያዎች ነን ማለት እንደሚገባውም ተናግረዋል፡፡ አያይዘውም ይህ ሥራ የመጨረሻችሁ ሳይኾን የመጀመሪያችሁ ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ከእናንተ ጋር ናቸው፡፡ ከአባቶቻችሁ መመሪያ እየተቀበላችሁ ከዚህ የበለጠ እንድታገለግሉ አደራ እላለሁ የሚል አባታዊ ምክር ሰጥተዋል፡፡

ሌሎች ብፁዓን አበውም ማኅበረ ቅዱሳንን አስነሥቶ ሕዝበ ክርስቲያኑን በዚህ መልኩ እንዲሰባሰብና ስለ ቤተ ክርስቲያኑ፣ ስለ ሃይማኖቱ እንዲማር በማድረጉ እግዚአብሔርን አመስግነዋል፤ በማኅበሩ ሥራ መደሰታቸውንም ገልጸዋል፡፡ ለወደፊትም ከአባቶች ጋር በመመካከር ከዚህ የበለጠ መትጋት እንደሚገባ አባታዊ ምክራቸውን አስተላልፈዋል፡፡

አንዳንድ ያነጋገርናቸው ምእመናን እንደገለጹልን በዝግጅቱ ከመደሰታቸው የተነሣ ከቤተሰቦቻቸውና ከልጆቻቸው ጋር በመኾን ስድስቱን ቀን በሙሉ በዐውደ ርእዩ ተሳትፈዋል፡፡ በዐውደ ርእዩ መሳተፍ የሚኖረውን ጠቀሜታ አስመልክቶ ቃለ መጠይቅ ያደርግንላቸው ምእመናንም ዐውደ ርእዩ ኹሉም ምእመን ስለ ሃይማኖቱ፣ ስለ ቤተ ክርስቲያኑና ስለ አገሩ ታሪክ እውቀት እንዲኖረው ከማድረጉ በተጨማሪ ራሱን እንዲያይና ድርሻውን በማወቅ የሚጠበቅበትን ሓላፊነት እንዲወጣ የሚያስችል ግንዛቤ ያስጨብጠዋል ብለዋል፡፡

ከአስተያየት መስጫ መዛግብት ላይ ከሰፈሩ ዐሳቦች ውስጥም ዐውደ ርእዩ በጣም አስተማሪ መኾኑን ገልጸው፣ የአዘጋጆቹን፣ የአስተናጋጆቹንና የገላጮቹን ጥንካሬ በማድነቅ እንደዚህ ዓይነቱ ዐውደ ርእይ በዐዲስ አበባ ከተማ ብቻ ሳይኾን፣ በየክፍለ ሀገሩና በየወረዳው መዘጋጀት እንደሚገባው፤ ትዕይንቶቹም ቀለል ባለ መልኩ በብሮሸርና በሲዲ መልክ ለምእመናን መዳረስ እንደሚኖርባቸው አስተያየት የሰጡ ሰዎችን ዐሳብ በአብዛኛው አንብበናል፡፡ በተጨማሪም ማኅበሩ በዐውደ ርእዩ ላይ የበጎ አድራጎት ማኅበራት ሥራዎች እንዲተዋወቁ ማድረጉ ያስመሰግነዋል፤ ለወደፊቱ እንደዚህ ዓይነት ዐውደ ርእይ ሲያዘጋጅ ከቤተ ክህነትና ከሰንበት ትምህርት ቤቶች ጋር በጋራ ቢሠራ ደግሞ የበለጠ ውጤታማ ይኾናል የሚሉና ሌሎችም አስተያየቶች ተሰጥተዋል፡፡

በአንጻሩ የዐውደ ርእዩ ጊዜ ጠባብ መኾኑ፣ ማኅበሩ ኤግዚብሽን ማዕከሉ ውስጥ ለታዳሚዎች የሚኾን ምግብ ቤት ስላልተዘጋጀ፣ እንደዚሁም በትዕይንቶቹ አዳራሾች ውስጥ ጎብኝዎቹ ስለሚደራረቡና የልዩ ልዩ ትዕይንቶች ገላጮች ድምፅ ስለሚቀላቀል ለወደፊቱ ሰፊ ዝግጅት ያስፈልገዋል ብለዋል፡፡ ከዚህ በተለየ ደግሞ ማኅበሩ ራሱን የሚያስተዋውቅበት የትዕይንት ክፍል ማዘጋጀት ነበረበት የሚል አስተያየት በጽሑፍም በቃልም ተነሥቷል፡፡

ከውጪ አገር ከመጡ ጎብኝዎች መካከል ማርቆስ ሀይዲኛክና ባለቤቱ አገራቸው ቡልጋርያ በሃይማኖታቸውም የምሥራቅ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን አባል መኾናቸውን ጠቅሰው በዚህ ዐውደ ርእይ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ታሪክና ሥነ ጽሑፋዊ ጥበብ፣ የክርስቲያኖቹን ትጋትና መንፈሳዊ ሕይወት እንደዚሁም የአገሪቱን ሕዝብ ባህል እንደተረዱበት ለዝግጅት ክፍላችን ገልጸዋል፡፡

ከሌላ ቤተ እምነት ከመጡ ግለሰቦች መካከልም ማርሺያ ሲንግልተን የምትባል አንዲት አሜሪካዊት የፕሮቴስታንቲዝም እምነት ተከታይ በዚህ ዐውደ ርእይ በመሳተፏ እድለኛ መኾኗን ጠቅሳ በጉብኝቱም የኢትዮጵያ ኦርቶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በታሪክ የበለጸገና በመጽሐፍ ቅዱሳዊ አስተምህሮ ላይ የተመሠረተ መኾኑን ከገለጸች በኋላ ዐዲስ እውቀት እንዳገኝ ስላደረጋችኹኝ አመሰግናለሁ የሚል አስተያየቷን በእንግሊዝኛ ቋንቋ አስፍራለች፡፡

በተያያዘ ዜና አንድ ጣልያናዊ ጎልማሳ የእስልምና ሃይማኖት ተከታይ በዐውደ ርእዩ የኢትየጵያን ታሪክና የክርስትናን አስተምህሮ እንደተረዳበትና በመታደሙም ደስተኛ እንደኾነ ገልጾ፣ ዐውደ ርእዩ በርካታ ምሁራን የተሳተፉበት መኾኑን ከትዕይንቶቹ ይዘት መረዳቱን ከተናገረ በኋላ ማኅበሩንና አዘጋጆቹን አመስግኗል፡፡

በመጨረሻም በትናንትናው ዕለት ከምሽቱ 4፡00 ዐውደ ርእዩ ሲጠናቀቅ የማኅበሩ ሥራ አስፈጻሚዎች፣ የዝግጅቱ አስተባባሪዎች፣ የትዕይንት ገላጮች፣ የአብነት ተማሪዎችና ሌሎችም ድጋፍ ሰጪ አካላት በኤግዚብሽን ማዕከሉ ግቢ ውስጥ ተሰባስበው ንሴብሖ ለእግዚአብሔር ስቡሐ ዘተሰብሐ እያሉ በሰላም ያስፈጸማቸውን ልዑል አግዚአብሔርን በዝማሬና በዕልልታ አመስግነዋል፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማእከል

ግንቦት ፳፫ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅድስት፣ አሐቲ፣ ከኹሉ በላይ የኾነች፣ በክርስቶስ ደም የተመሠረተች፣ በቅዱሳን ነቢያት ትንቢት የጸናች፣ በቅዱሳን ሐዋርያት ስብከት የታነፀች፣ በሊቃውንት አስተምህሮ የጸናች፣ በምእመናን ኅብረት የተዋበች ንጽሕት ማኅደረ ሃይማኖት ናት፡፡

የዚህችን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ምእመናን ይረዱ ዘንድ ልዩ ልዩ ዘዴዎችን መጠቀም ይገባል፡፡ ከእነዚህ ዘዴዎች አንዱ ከሰሞኑ በማኅበረ ቅዱሳን አማካይነት በአዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል ለዕይታ ቀርቦ የሰነበተው ዓይነት ዐውደ ርእይ አንዱ ነው፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን አምስተኛውን ዐውደ ርእይ ለምእመናን ሊያቀርብ የነበረው ከመጋቢት ፲፭-፳፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም የነበረ ቢኾንም ዳሩ ግን ዐውደ ርእዩ በሰዓቱ ግልጽ ባልነበረ ምክንያት ላልተወሰነ ጊዜ ታግዶ ከቆየ በኋላ እግዚአብሔር ሥራውን የሚሠራበት ጊዜ ሲደርስ እነሆ ከግንቦት ፲፯ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ጀምሮ በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል ለተመልካቾቹ ይፋ ኾነ፡፡

በዚህ ዐውደ ርእይ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መሠረተ እምነት፣ ዶግማ፣ ቀኖና እና ትውፊት በሰፊው ቀርቦ በምእመናን ሲታይ ሰንብቷል፡፡ በተጨማሪም በአንድነት ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገልና የተቸገሩትን ለመርዳት የጎላ ድርሻ ያላቸው የጽዋ፣ የበጎ አድራጎትና የጉዞ ማኅበራት አገልግሎትም ተዳስሷል፡፡

ሊቃውንቱና ደቀ መዛምርቱ በዐውደ ርእዩ የሚሳተፉትን ጎብኝዎች ለማስደሰት የአገር ርቀት ሳይገድባቸው፣ መንገድ ሳያደክማቸው ከየመኖሪያ ቦታቸው በመምጣት በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል ለሳምንት ያህል ቆይተዋል፡፡

ዐውደ ርእዩ በአራት ዐበይት አርእስት ማለትም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መሠረተ እምነት፣ የቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ ተልዕኮ፣ የቤተ ክርስቲያን ተጋድሎ እና ምን እናድርግ በሚሉ የተከፋፈለ ሲኾን በእያንዳንዱ ትዕይንት ሥርም በርካታ አርእስት ተካተውበታል፡፡ እያንዳንዳቸው የያዟቸው ጭብጦችም የሚከተሉት ናቸው፤

ትዕይንት አንድ፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መሠረተ እምነት

ይህ ትዕይንት ሀልዎተ እግዚአብሔር፣ ነገረ ድኅነት፣ ነገረ ማርያም፣ ነገረ ቅዱሳን እና ነገረ ቤተ ክርስቲያን የሚዳሰሱበት ክፍል ሲኾን፣ በውስጡም ሀልዎተ እግዚአብሔር፣ እግዚአብሔር አምላክ በጊዜና በቦታ የማይወሰን፣ መጀመሪያና መጨረሻ የሌለው፣ የፍጥረታት ኹሉ አስገኚና እርሱ በገለጠው መጠን ብቻ የሚታወቅ እንጂ ባሕርዩ ተመርምሮ ሊደረስበት እንደማይቻል እንደዚሁም መልዕልተ ኵሉ (የኹሉ የበላይ) መኾኑን ያስረዳል፡፡

እግዚአብሔር ሲባልም አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ማለት እንደኾነ፤ እንደዚሁም እግዚአብሔር አምላክ በሥነ ፍጥረቱ፣ በአምላካዊ መግቦቱ፣ በሕሊና፣ በቅዱሳት መጻሕፍት፣ በዓለም ላይ በሚፈጸሙ ድርጊቶች ምስክርነት፣ ሥጋን በመልበስራሱን ለእኛ እንደገለጠልን በዚህ ትዕይንት ተብራርቷል፡፡

በተጨማሪም ሃይማኖት ማለት እግዚአብሔር ራሱን ለሰው ልጅ የገለጠበት መንገድ ስለመኾኑና ስለ አብርሃም እግዚአብሔርን ፈልጎ ማግኘት፣ በተጨማሪም በዓለም ላይ ብዙ ሃይማኖቶች ለመኖራቸው ምክንያቱ የሰይጣን ክፉ ሥራና የሰው ልጅ የመረዳት ዓቅም መለያየት ስለመኾኑ ተብራርቶበታል፡፡

ነገረ ድኅነት ደግሞ በአዳምና በሔዋን ምክንያት የዘለዓለም ሞት ተፈርዶበት የነበረው የሰው ልጅ ከሦስቱ አካላት አንዱ በኾነው በጌታችን በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሕማማተ መስቀልና ሞት የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ መቻሉን በማስረዳት እመቤታችን የመልአኩን ብሥራት ከሰማችበት ጊዜ ጀምሮ የጌታችን ፅንሰት፣ ልደት፣ስደት፣ ዕድገት፣ ጥምቀት፣ ትምህርት፣ ተአምራት፣ ሕማማት፣ ሞት፣ ትንሣኤ፣ ዕርገትና ዳግም ምጽአት የነገረ ድኅነት መሠረቶች መኾናቸውን ይተነትናል፡፡

እንደዚሁም እምነት፣ ምግባር እና ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያንን መፈጸም የሰው ልጆች ለመዳን ሊያሟሏቸው የሚገቡ ቅድመ ኹኔታዎች መኾናቸው በዚህ ርእስ ሥር ተካቷል፡፡

ነገረ ማርያምም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የአምላክ እናት እንደመኾኗ ከመፅነሷ በፊት፣ በፅንሷ ጊዜም ኾነ ከፀነሰች በኋላ ዘለዓለም ድንግል ስለመኾኗ እንደዚሁም በእግዚአብሔር ፊት ቆማ ለእኛ እንደምታማልድ ያስረዳል፡፡

ነገረ ቅዱሳን ደግሞ ሰማያውያን መላእክትን ጨምሮ ያላቸውን ኹሉ ትተውእግዚአብሔርን ብቻ የተከተሉ፣ መከራ መስቀሉን ተሸክመው ሕይዎታቸውን በሙሉበ ተጋድሎ ያሳለፉ፣ በፍጹም ልቡናቸው ጸንተው እስከ መጨረሻው ድረስ እግዚአብሔርን የተከተሉቅዱሳን አባቶች እና እናቶች ከእግዚአብሔር በተሰጣቸው ጸጋና ሥልጣን በምድርም በሰማይም እንደሚያማልዱ ያስረዳል፡፡

በነገረ ቤተ ክርስቲያን ሥር ደግሞ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የጌታችን የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስአካል፣ የምእመናን ኅብረት፣ የሰው ልጆችና የመላእክት፣ በዓለመ ሥጋና በዓለመ ነፍስ ያሉ እንደዚሁም የሥውራንም የገሃዳውያንም (በግልጽ የሚታዩ)ምእመናን አንድነትመኾኗ፣ ይህቺ ቤተ ክርስቲያን በተጋድሎ ብትኖርም ነገር ግን ድል አድራጊ፤ በባሕርዩአም ቅድስት፣ አሐቲ (አንዲት)፣ ሐዋርያዊት፣ ኵላዊት እንደኾነች ተተንትኖበታል፡፡

ትዕይንት ሁለት፡- የቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ ተልእኮ

በዚህ ትዕይንት የሐዋርያነትና የሐዋርያዊ አገልግሎት ትርጕም፣ ዓላማና አመሠራረትን ጨምሮ ስብከተ ወንጌል አንዴት እንደ ተስፋፋና እስከ ዛሬ ድረስ በቤተ ክርስቲያን ላይ የደረሱ ፈተናዎችና መልካም አጋጣሚዎች የተካተቱበት ልዩ ልዩ መረጃና ትምህርት ቀርቦበታል፡፡

የሐዋርያዊ አገልግሎት መጀመርና መስፋፋት በኢትዮጵያ በሚለው የዚህ ትዕይንት ንዑስ ርእስ ሥር ከ፩ኛው እስከ ፯ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ድረስ የነበረው ሐዋርያዊ አገልግሎት ተዳሶበታል፡፡ የአባ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን፣ የቅዱሳን ነገሥታት አብርሀ እና አጽብሀ፣ የዘጠኙ ቅዱሳን፣ የዐፄ ካሌብና የቅዱስ ያሬድ ሐዋርያዊ አገልግሎት ለስብከተ ወንጌል መስፋፋት ያደረገው አስተዋፅዖ በርእሱ የተገለጡ የታሪክ ክፍሎች ናቸው፡፡

ሁለተኛው ንዑስ ርእስ ደግሞ ከ፰ኛው እስከ ፲ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ድረስ በዮዲት ጉዲት ምክንያት ቅዱሳት መጻሕፍትና አብያተ ክርስቲያናት በመቃጠላቸው፣ ሊቃውንቱና ምእመናኑ በመገደላቸውና በመሰደዳቸው በቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ አገልግሎት ላይ ጉዳት እንደ ደረሰ ያስረዳል፡፡

በሦስተኛ ደረጃ በዮዲት ጉዲት ዘመን በደረሰው በደል ቁጭት ያደረባቸው አባቶች በመነሣታቸው ምክንያት ከዐሥራ ፲፩ኛው እስከ ፲፮ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የነበረውን የሐዋርያዊ ተልዕኮ ትንሣኤ በመግለጽ ለዚህም የአራቱ ቅዱሳን ነገሥታት (ይምርሃነ ክርስቶስ፣ ሐርቤ/ገብረ ማርያም፣ ላሊበላና ነአኵቶ ለአብ) መነሣት፤ የሐይቅ እስጢፋኖስ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ገዳም መመሥረትና እንደ አቡነ ተክል ሃይማኖት ያሉ አባቶች፣ እንደዚሁም በዐፄ ዘርዐ ያዕቆብና በዘመኑ የነበሩ አበው የስብከተ ወንጌል አገልግሎት፤ በተጨማሪም እንደ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ያሉ ቅዱሳን መጻሕፍትን በማዘጋጀት ያበረከቱትን ከፍተኛ አስተዋፅዖ ይገልጻል፡፡

በትዕይንት ሁለት በአራተኛ ደረጃ የተቀመጠው ነጥብም ከ፲፯ኛው እስከ ፲፰ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ድረስ በነበረው ጊዜ በግራኝ አሕመድ ወረራ ምክንያት ጥንታውያን አብያተ ክርስቲያናትና ቅዱሳት መጻሕፍት በመቃጠላቸው፣ ሊቃውንቱና ምእመናኑ በግፍ በመጨፍጨፋቸው የተነሣ በሐዋርያዊ አገልግሎቱ ላይ የከፋ ጉዳት መድረሱን ይገልጻል፡፡

በተመሳሳይ መልኩ በዚያ ዘመን ከባዕድ አገር የመጡ የሁለት አካል፣ ሁለት ባሕርይ አማኞች ተፅዕኖ ቢበረታም ተከራክረው መርታት የሚችሉና ለሃይማኖታቸው ሲሉ አንገታቸውን የሚሰጡ አባቶችና እናቶች የተገኙበት ወቅት እንደነበረም ተጠቅሷል፡፡ በዘመነ መሣፍንት በአገራችን ተስፋፍቶ የነበረውን የሁለት አካል ሁለት ባሕርይ አስተሳሰብ ተከትሎ በተፈጠረው የጸጋና የቅብዓት ትምህርት የተከሠተዉን ችግር ለመፍታት ከፍተኛ ጥረት መደረጉም ተገልጿል፡፡

በዚሁ ትዕይንት በአምስተኛ ደረጃ የተቀመጠው ነጥብም ከ ፲፱ኛው እስከ ፳ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ድረስ የነበረውን ሐዋርያዊ አገልግሎት የሚያስቃኝ ሲኾን፣ በውስጡም በዘመኑ መጽሐፍ ቅዱስ ከግእዝ ወደ አማርኛ መተርጐሙ፣ በግዳጅ ተይዘው ወደ ሌላ ሃይማኖት ሔደው የነበሩ ምእመናን ወደ ክርስትና መመለሳቸው፣ እንደዚሁም የነመምህር አካለ ወልድ እና መልአከ ሰላም አድማሱ መነሣት ለቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ ተልዕኮ መፋጠን መልካም አጋጣሚ እንደ ነበረ ያስረዳል፡፡

በተጨማሪም ቅዱስ ሲኖዶስ መቋቋሙ፣ የካህናት ማሠልጠኛዎችና መንፈሳውያን ኰሌጆች መመሥረታቸው፣ የሰበካ ጉባኤ መዋቅር መዘርጋቱ፣ ወጣቶች በሰንበት ትምህርት ቤቶችና በማኅበራት አገልግሎት መስጠት መጀመራቸው፣ የምእመናን መንፈሳዊ ተሳትፎ መጨመሩ፣ በውጭዎቹ ክፍላተ ዓለም አብያተ ክርስቲያናት መታነፀቸው እንደዚሁም ቤተ ክርስቲያናችን መገናኛ ብዙኃንና በአፍ መፍቻ ቋንቋ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት መስጠት መጀመሯ በተለይ ፳ኛውን መቶ ክፍለ ዘመን ለሐዋርያዊ ተልዕኮ የተመቸ እንዲኾን ማድረጋቸው ተብራርቶበታል፡፡

በትዕይንት ሁለት የመጨረሻው ርእስ ላይ ደግሞ በአሁኑ ሰዓት የቴሌቭዥንና የሌሎችም መገናኛ ዘዴዎች ሥርጭት አለመኖር፣ በልዩ ቋንቋዎች የሚያስተምሩ ሰባክያንና ካህናት እጥረት እንደዚሁም በየቋንቋው የቅዱሳት መጻሕፍት በበቂ ኹኔታ አለመታተም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ አገልግሎት ውሱንነት መገለጫዎች መኾናቸው ተጠቅሷል፡፡

ትዕይንት ሦስት፡- የቤተ ክርስቲያን ተጋድሎ

ይህ ትዕይንት ቤተ ክርስቲያን ወንጌልን ለማስፋፋት ያሳለፈችውን ተጋድሎ፣ የመናፍቃንን ተፅዕኖና የሰማዕታትን ታሪክ፣ የተዋሕዶ ሃይማኖትን አስተምህሮ ለማስጠበቅ የተደረጉ ልዩ ልዩ ዓለም ዓቀፍና አገር ዓቀፍ ጉባኤያትን በዝርዝር የያዘ ሲኾን፣ በኃይል ሃይማኖቱን ለማጥፋት ይተጉ በነበሩ አካላት ምክንያት ቤተ ክርስቲያን ስላደረገችው ተጋድሎ፣ ስለ ቅዱስ እስጢፋኖስ ሰማዕትነትና በዘመነ ሰማዕታት በክርስቲያኖች ላይ ስለደረሰው መከራ፣ እንደዚሁም በርካታ ክርስቲያኖች በሰማዕትነት ስለማለፋቸው፣ በተጨማሪም ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ተነሥቶ ክርስቲያኖች ዕረፍት ስለማግኘታቸው የሚያትት ዐሳብ ይዟል፡፡

ይህ የትዕይንት ክፍል በአገራችን በኢትዮጵያም እንደ ዮዲት ጉዲት፣ ግራኝ አሕመድ፣ ዐፄ ሱስንዮስ፣ ፋሽስት ጣልያን፣ ያሉ ጠላቶች በቤተ ክርስቲያን ላይ ያደረሱት ጉዳት ተጠቅሷል፡፡ ቀጥሎም የዘመናችን ሰማዕታት በሚል ንዑስ ርእስ ሃይማኖታችንን አንክድም፣ ባዕድ አናመልክም ያሉ ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖች በ፲፱፻፺፱ ዓ.ም በጂማ ሀገረ ስብከት በበሻሻ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ቤተ ክርስቲያን፤ በቅርቡ በ፳፻፯ ዓ.ም ደግሞ በሊብያ በረሃና በሜዴትራንያን ባሕር ዳርቻ በግፍ የተገደሉ የግብፅ፣ የኢትዮጵያና የሌሎችም አብያተ ክርስቲያናት ሰማዕታትን ይዘክራል፡፡

በቃልም በጽሑፍም በሚበተኑ የሐሰት ትምህርቶች ምክንያት ቤተ ክርስቲያን የፈጸመችውን ተጋድሎ በማውሳት በዚህ የተነሣም ልዩ ልዩ ጉባኤያት መደረጋቸውን ይዘረዝራል፡፡ በዚህ መሠረት ከአይሁድ ወደ ክርስትና ሃይማኖት በመጡትና በቀደሙ ክርስቲያኖች መካከል የልዩነት ትምህርት በመከሠቱ ቅዱሳን ሐዋርያት በ፶ ዓ.ም በኢየሩሳሌም ጉባኤ ማድረጋቸውንና ከዚያ ጊዜ ጀምሮ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ እንደ ተመሠርተ ይገልጻል፡፡

በማያያዝም ሦስቱን ዓለም ዓቀፍ ጉባኤያትን (ጉባኤ ኒቅያ፣ ጉባኤ ቍስጥንጥንያ እና ጉባኤ ኤፌሶን) በማንሣት ውሳኔዎቻቸውን አስቀምጧል፤ ይኸውም፡- በ፫፳፭ ዓ.ም ፫፻፲፰ቱ ሊቃውንት አርዮስን ለማውገዝ በኒቅያ ባደረጉት ጉባኤ ጸሎተ ሃይማኖትን (መሠረተ እምነት) ማርቀቃቸውን፤ በ፫፹፩ ዓ.ም ፻፶ው ሊቃውንት መቅዶንዮስን ለማውገዝ በቍስጥንጥንያ ባደረጉት ጉባኤ ወነአምን በመንፈስ ቅዱስ እግዚእ ወማኅየዊ ዘሠረጸ እምአብ፤ ጌታ፣ ማኅየዊ በሚኾን ከአብ በሠረጸ በመንፈስ ቅዱስ እናምናለን የሚለው ሐረግ በጸሎተ ሃይማኖት መካከተቱን፤ በ፬፴፩ ዓ.ም ደግሞ ፪፻ ሊቃውንት ንስጥሮስን አውግዘው በአንዲት የተዋሕዶ ሃይማኖት የሚያጸና ትምህርት ማስተማራቸውን ያትታል፡፡

በተጨማሪም በአገራችን በኢትዮጵያ በሃይማኖት ምክንያት በዐሥራ አምስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን የሰንበትን አከባበር አስመልክቶ በቤተ ኤዎስጣቴዎስና በቤተ ተክለ ሃይማኖት መካከል የተፈጠረውን አለመግባባት ለመፍታት በ፲፬፻፶ ዓ.ም በደብረ ምጥማቅ በዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ አማካኝነት ጉባኤ ተደርጎ ሁለቱም ሰንበታት እኩል ይከበሩ የሚል ውሳኔ ስለመተላለፉ፤ ነሐሴ ፲፫ ቀን ፲፰፻፵፮ ዓ.ም በጎንደር ክፍለ ሀገር በደብረ ታቦር ከተማ አምባጫራ በተባለ ቦታ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አባቶች ከቅባትና ከጸጋዎች ጋር የሃይማኖት ጉባኤ አድርገው ጸጋና ቅባቶች ስለመረታታቸው፤ የቅባትና የጸጋ ትምህርት ፈጽሞ ባለመጥፋቱ ግንቦት ፳፩ ቀን ፲፰፻፸፭ ዓ.ም በደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት በቦሩ ሜዳ በድጋሜ ከቅባትና ከጸጋዎች ጋር የሃይማኖት ጉባኤ ተደርጎ ቅባትና ጸጋ ተረተው የተዋሕዶ ሃይማኖት ስለመጽናቷ ይገልጻል፡፡

በመጨረሻም የመናፍቃን ሰርጎ ገብነትና የተሐድሶ መናፍቃን ዘመቻዎች የዘመናችን የቤተ ክርስቲያን ፈተናዎች መኾናቸው በዚህ ትዕይንት ከማስረጃ ጋር ቀርቧል፡፡

ትዕይንት አራት፡- ምን እናድርግ?

ይህ ትዕይንት ደግሞ ምእመናን በዐውደ ርእዩ ከተመለከቷቸውና ከሰሟቸው እውነታዎች በመነሣት የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ከመጠበቅና ድርሻቸውን ከማወቅ አኳያ ልዩ ልዩ ችግሮችን ለመቅረፍ ወደፊት ምን ማድረግ እንደሚጠበቅባቸው የሚያስረዱ መረጃዎችን አካቷል፡፡

የመጀመሪያው ነጥብ ሐዋርያዊ ተልዕኮን የተመለከተ ሲኾን በርእሱም በ፲፬ አህጉረ ስብከት፣ በ፯፻፳ አጥቢያዎች በተደረገ ጥናት ፫፵፮ አብያተ ክርስቲያናት መዘጋታቸው፣ ፪፻፺፮ቱ አገልጋይ ካህናት እንደሌሉባቸው፣ ፻፷፰ቱ ደግሞ በዓመት/በወር አንድ ጊዜ ብቻ ቅዳሴ የሚቀደስባቸው እንደኾኑ ያስረዳል፡፡

በተያያዘ መረጃ ከ፲፱፻፹፬-፳፻ ዓ.ም ድረስ ባለው ጊዜ ውስጥ ብቻ ሰባት ሚልየን ሰባት መቶ ሰባ ስድስት ሺሕ ሁለት ሃያ ስድስት ምእመናን ወደ ሌሎች ቤተ እምነቶች መወሰዳቸው፣ እንደዚሁም በአዲስ አበባ እና በሌሎች አብያተ ክርስቲያናት መካከል ያልተመጣጠነ የአገልጋዮች ሥርጭት መኖሩ በዚህ ርእስ ሥር ተገልጿል፡፡

በትዕይንት አራት ሌላው ነጥብ የመገናኛ ብዙኃን አጠቃቀም ንጽጽር ሲኾን በንጽጽሩም የግብፅ ኦርቶዶስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፻፴፬ የመካነ ድር፣ ፲፩ የቴሌቭዥን እና ፲ የሬድዮ ሥርጭት ሲኖራት፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ግን ፲፪ የመካነ ድር፣ ፪ የሬድዮ፣ እና ፩ የቴሌቭዥን ሥርጭት ብቻ እንዳላት ተጠቅሷል፡፡

ሁለተኛው የትዕይንት አራት ጭብጥ ደግሞ ገዳማትና የአብነት ትምህርት ቤቶች በመተዳደሪያ ዕጦት፣ በድርቅ፣ በመዘረፍ፣ በበሽታ፣ ወዘተ የመሰሉ ችግር ውስጥ መውደቃቸውን ያስረዳል፡፡

በዚህ ትዕይንት ሦስተኛው ነጥብ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ያልተቋቋሙባቸው አጥቢያዎች መኖርና ያሉትም በቂ አለመኾናቸው፣ የሰባክያነ ወንጌል እጥረትና ግቢ ጉባኤያት ያልተመሠረቱባቸው የትምህርት ተቋማት መኖራቸው ቤተ ክርስቲያን ካጋጠሟት ችግሮች መካከል እንደሚጠቀሱ ይናገራል፡፡

በአራተኛ ደረጃ የተቀመጠው ነጥብ እንደሚያስረዳው የንስሐ አባትና የንስሐ ልጆች ግንኙነት መላላት፣ የምእመናንን መንፈሳዊ የእርስበርስ ግንኙነት (ፍቅር) መቀነስ እንደዚሁም ችግሩ እኔን አይመለከተኝም ብለው የሚያስቡ ምእመናን መበራከት ከቤተሰብና ከማኅበራዊ ኑሮ አኳያ ቤተ ክርስቲያን ያጋጠሟት ችግሮች ናቸው፡፡

በአምስተኛ ደረጃ ከተቀመጠው ነጥብ እንደምንገነዘበው ደግሞ ውጤት ተኮር ዕርዳታ የመስጠት ችግር፣ በልዩ ልዩ ሱስና በአእምሮ ሕመም የተጠቁ ምእመናንን ማገዝ አለመቻሉ፣ ውስን በኾኑ የልማት ሥራዎች ላይ ማተኮር ቤተ ክርስቲያን በማኅበራዊ አገልግሎትና በልማት የጋጠሟት ችግሮች ናቸው፡፡

እነዚህን ከላይ የተዘረዘሩትንና መሰል ችግሮችን ለመቅረፍ በጠቅላይ ቤተ ክህነት፣ በማኅበረ ቅዱሳን፣ በጽርሐ ጽዮን እና በደጆችሽ አይዘጉ ዓይነት ማኅበራት በስብከተ ወንጌልና በጥምቀት አገልግሎት፣ በሥልጠና፣ እንደዚሁም በሌላ ማኅበራዊና ልማታዊ እንቅስቃሴእየተደረገ ያለው ጥረት የሚበረታታ ቢኾንም ነገር ግን ይህ ብቻ በቂ ስላልኾነ ኹሉም የድርሻውን ቢወጣ የተሻለ ሥራ መሥራትና ለውጥ ማምጣት እንደሚቻል ይጠቁማል፡፡

ይህ ኹሉ ችግር በዚህ ከቀጠለ ቤተ ክርስቲያን ወደፊት በሚሊየን የሚቈጠሩ ምእመናንን፣ አገልጋይ ካህናትን፣ አርአያ የሚኾኑ ገዳማውያን መነኰሳትን ማጣት፤ በቤተሰብ ደረጃም ፍቅር የሌላቸውና ተስፋ የሌላቸው ወጣቶች እንዲበዙ ያደርጋል፡፡

በአጠቃላይ ከላይ የተጠቀሱ ችግሮች በዚሁ ከቀጠሉ ቤተ ክርስቲያን በምጣኔ ሀብትም፣ በማኅበራዊ አገልግሎትና በሌሎችም ዘርፎች ዓቅም የሌላትና ተሰሚነት ያጣች ትኾናለች የሚለው ዐሳብ በትዕይንቱ የተገለጸ ሥጋት ነው፡፡

ከዚህ ቀጥሎ በሥዕል መልክ የተቀናበረው መልእክት እርስዎ የትኛው ነዎት? ያልተረዳ? ያንተ/ያንቺ ድርሻ ነው የሚል? ተወቃቃሽ? ሳይመረምር የሚከተል? ማሰብ ብቻ ሥራ የሚመስለው? ተስፋ የቈረጠ? አልሰማም፤ አላይም፤ አልናገርም የሚል? የሚያወራ፣ የሚተች፣ ግን የማይሠራ? ሲል ይጠይቃል፡፡ የትዕይንቱ ማጠቃለያም ምን እናድርግ? በሚል ርእስ አራት የመፍትሔ አቅጣጫዎችን አስቀምጧል፤

፩. የክርስቶስ አካል በኾነችው ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሕያው አካል እንኹን፤

፪. ቤተ ክርስቲያንን በመሰለን ብቻ ሳይኾን በኾነችው እንወቃት፤ እንረዳትም፤

፫. ስለ ቤተ ክርስቲያን ያገባኛል፤ ይመለከተኛል ብለን እንሥራ፤

፬. ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው የኾነውና የማዳን ተግባሩን ኹሉ የፈጸመው ለሰው ልጅ ነው፤

ሰው! ሰው! ሰው!

ኑ፤ አብረን እንሥራ፤ ለውጥም እናመጣለን የሚለው ኃይለ ቃልም እንደማንቂያ ደወል የተቀመጠ መልእክት ነው፡፡

ዐውደ ርእዩ ከነዚህ ዐበይት ትዕይንቶች በተጨማሪ የሕፃናት ትዕይንትም የተካተተበት ሲኾን፣ በዚህ ትዕይንት ለሕፃናት አእምሮ የሚመጥኑ መንፈሳውያን ትምህርቶች ተዘጋጅተውበታል፡፡

በትዕይንቱ ውስጥም የአዳምና የሔዋን ታሪክ፣ ነገረ ድኅነት እና ነገረ ቅዱሳን በሥዕላዊ መግለጫ ቀርቧል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የቤተ ክርስቲያን የዜማ መሣሪያዎችና ንዋያተ ቅድሳት፣ እንደዚሁም ፊደለ ሐዋርያና ሌሎችም የልጆችን ስሜት ሊያስደስቱ የሚችሉ የትዕይንቱ ክፍሎች ተዘጋጅተዋል፡፡ ሕፃናቱም ክፍሉ ውስጥ እየዘመሩ ይማራሉ፤ ይደሰታሉ፡፡

ከሁሉም በተለየ መንገድ ደግም ከቍጥር ፩ አዳራሽ በስተሰሜን አቅጣጫ ካሉት ዛፎች ሥር ጊዜያዊ ጎጆ ቀልሰው የሚገኙት የሁሉም ገባኤያት (የንባብ፣ የዜማ/የድጓ፣ የቅዳሴ፣ የቅኔ፣ የአቋቋም፣ የመጻሕፍትና የአቡሻሕር ጉባኤ ቤቶች) መምህራን ደቀ መዛሙርታቸውን በተግባር ሲያስተምሩመታየታቸው የኤግዚብሽን ማዕከሉን የኹሉም ጉባኤያት መገኛ ገዳም አስመስሎታል፡፡

የንባብ ተማሪዎች ከመምህራቸው ከመምህር ተክለ ጊዮርጊስ ደርቤ እግር ሥር ቁጭ ብለው መጽሐፎቻቸውን በአትሮንሶቻቸው ዘርግተው ተነሽ፣ ተጣይ፣ ወዳቂና ሰያፍ ሥርዓተ ንባብን ለመለየት ይችሉ ዘንድ ተጠንቅቀው ያነባሉ፡፡

የቅዳሴ ደቀ መዛሙርት ከመጋቤ ስብሐት ነጋ፤ የዜማ/የድጓ ደቀ መዛሙርት ደግሞ ከሊቀ ምሁራን ይትባረክ ካሣዬ፤ የዝማሬ መዋሥዕት ደቀ መዛሙርትም ከመጋቤ ብርሃናት ፈንታ አፈወርቅ እግር ሥር ቁጭ ብለው ትልልቅና ባለምልክት የዜማ መጻሕፍቶቻቸውን በአትሮንሶቻቸው ላይ አስቀምጠው በግዕዝ፣ ዕዝልና በዓራራይ በተመሠረተው የቅዱስ ያሬድ ሰማያዊ የዜማ ሥርዓት መሠረት ያዜማሉ፤ መምህራኑም እርማት ይሰጣሉ፡፡

የቅኔ ደቀ መዛሙርትም አንድም ግስ በማውረድ፣ አንድም ከመምህራቸው ፊት ኾነው ቅኔ በመንገርና በማሳረም፣ አንድም መምህራቸው የዘረፉላቸውን ቅኔዎች በመቀጸል ግቢውን አድምቀውታል፡፡ የአቋቋም ደቀ መዛሙርት ደግሞ ከመምህራቸው ከመምህር ዮሐንስ በርሄ ፊት ለፊት ክብ ሠርተው በመቀመጥ በዕለቱ የሚቀጽሉትን ቃለ እግዚአብሔር በጣቶቻቸው እያጨበጨቡ፣ በእግሮቻቸው እያሸበሸቡ ሲያዜሙ የንጋት አዕዋፍን ዝማሬ ያስታውሳሉ፡፡

የአቡሻሕርና የድጓ መምህር የኾኑት መጋቤ አእላፍ ወንድምነው ተፈራም እርጅና ሳይበግራቸው የዘመናት፣ የበዓላት፣ የዕለታትና የአጽዋማት ማውጫ ቀመር የኾውን የባሕረ ሐሳብ ትምህርት ለደቀ መዛሙርታቸው በማስቀጸል ላይ ናቸው፡፡ መምህር ዘለዓለም ሐዲስም የመጻሕፍት ትርጓሜ ደቀ መዛሙርታቸውን ከፊት ለፊታቸው አስቀምጠው ብሉዩንም፣ ሐዲሱንም፣ ሊቃውንቱንም፣ መነኰሳቱንም ለደቀ መዛሙርታቸው ይተረጕማሉ፡፡

ምን ይኼ! ብቻ የብራና መጻሕፍት አዘገጃጀትም የጉብኝቱ አካል ኾኖ ሰንብቷል፡፡ ከዚህ ሌላ ለትዕይንቱ መጨረሻ ከኾነው አዳራሽ ውስጥ ከሚጎበኙ የማኅበሩ ልዩ ልዩ ክፍሎች መካከል አንዱ በኾነው የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ ፕሮግራም የትዕይንት ክፍል ውስጥ ከጠረፋማ አከባቢዎች የመጡትና የአብነት ትምህርት በመማር ላይ የሚገኙት ሕፃናት ሴቶችና ወንዶች ብትፈልጉ ውዳሴ ማርያም፣ ቢያሻችሁ ደግሞ መልክዐ ማርያም ያነበንቡላችኋል፡፡ ይህም ቤተ ክርስቲያናችን በብሔር፣ በዘር፣ በቀለም፣ በጎሣና በጾታ ሳታበላልጥ የማይነጥፈውን መንፈሳዊ እውቀቷን ለኹሉም እንደምታካፍል አመላካች ነው፡፡

በልማት ተቋማት አስተዳደር ተዘጋጅተው ለሽያጭ የቀረቡት ንዋያተ ቅድሳት (መንበር፣ ልብሰ ተክህኖ፣ አክሊል፣ መጎናጸፊያ፣ ጽንሐሕ/ጽና፣ ቃጭል፣ ወዘተ) እንደዚሁም የቤተ ክርስቲያን የዜማ መሣሪያዎች በሥርዓት ተደርድረው እዩን፤ እዩን፤ ግዙን፤ ግዙን ይላሉ፡፡ ቅዱሳት መጻሕፍቱም እንደዛው፡፡

ከዐውደ ርእዩ ጎን ለጎን ከምሽቱ 11፡00 ጀምሮ የንባብ፣ የቅዳሴና የሰዓታት፣ የአቋቋምና የዝማሬ መዋሥዕት፣ ባሕረ ሐሳብ (የአቡሻኽር ትምህርት)፣ ቅኔ፣ ትርጓሜ መጻሕፍት፣ ዜማ/ድጓ ምንነታቸውን፣ አገልግሎታቸውን፣ አቀራረባቸውንና ከቅዱሳት መጻሕፍት ጋር ያላቸውን ትስስር የሚያስረዱ ጥናቶች በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ሲቀርቡ ሰንብተዋል፡፡

ከዚህ በተጨማሪ እሑድ ግንቦት ፳፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ኦርቶዶክሳዊ አስተምህሮ ሙስናን ከመዋጋት አንጻር ያለው ሚና እና የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ወቅታዊ ፈተናዎችና መፍትሔዎቻቸው በሚሉ አርእስት በዐዲስ አበባ መንገድ ትራንስፖርት ባለሥልጣን አዳራሽ ከቀኑ 8፡00 ጀምሮ ሁለት ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበዋል፡፡

ባጠቃላይ በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽ ማዕከል በተዘጋጀው አምስተኛው የማኅበረ ቅዱሳን ዐውደ ርእይ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ተነቧል፤ ተተርጕሟል፤ ተብራርቷል፡፡ በዓለማዊ ጉዳዮች ተጨናንቆ የነበረው የኤግዚብሽን ማዕከሉ በመንፈሳዊ ትምህርትና ጣዕመ ዜማ ደምቆ ለስድስት ቀናት ያህል በመሰንበቱ እጅግ ተደስቷል፡፡ ዐውደ ርእዩ በድጋሜ ቢታይ የሚልም ይመስላል፡፡ ምክንያቱም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በአምስተኛው የማኅበረ ቅዱሳን ዐውደ ርእይ በዐዲስ አበባ ኤግዚአብሽን ማዕከል በግልጽ ታይታለችና፡፡ እርሷን ማየት፣ ትምህርቷንም መስማት፣ ጣዕመ ዜማዋን ማጣጣም እጅግ አስደሳች ነውና፡፡

ከላይ በገለጽነው መልኩ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ለምእመናን ሲያስረዳ የነበረው ይህ ዐውደ ርእይ ግንቦት ፳፪ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ከምሽቱ 4፡00 ገደማ በሰላም ተጠናቋል፡፡ ይህ ዐውደ ርእይ በእግዚአብሔር ኃይል፣ በቅዱሳን ተራዳኢነት በሚያስደስትና በሚማርክ መልኩ ያለምንም ችግር ተከናውኗል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

አምስተኛው የማኅበረ ቅዱሳን ዐውደ ርእይ በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል

ግንቦት ፳፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል ከፍ ብሎ የሚሰማው የመዝሙር ድምፅና በማዕከሉ መግቢያ በር ላይ የተለጠፉ መንፈሳውያን ማስታወቂያዎች አካባቢው አንዳች ብርቱ ጉዳይ እንዳለበት ይመሰክራሉ፡፡ ብዙ የቆሙ መኪኖች፣ በሺሕ የሚቈጠሩ ምእመናን መንገዱን አጨናንቀውታል፡፡

ከዐዲስ አበባ ከተማ ብቻ ሳይሆን ከልዩ ልዩ የኢትዮጵያ ክፍላተ አህጉር የሚመጡ ምእመናንና ምእመናት ከግንቦት 17 ቀን 2008 ዓ.ም ጀምሮ እግሮቻቸውን ወደ አንድ አቅጣጫ አድርገዋል፤ ወደ ዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል፡፡ የጉዟቸው ምክንያት ደግሞ የማኅበረ ቅዱሳን አምስተኛው ዙር መንፈሳዊ ዐውደ ርእይ፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ይህንን ዐውደ ርእይ ለማዘጋጀት ከዓመታት በፊት ዓቅዶ ሠርቷል፤ ዐውደ ርእዩ ለምእመናን ሊቀርብ የነበረውም ከመጋቢት 15-21 ቀን 2008 ዓ.ም የነበረ ቢኾንም ዳሩ ግን በሰዓቱ የእግዚአብሔር ፈቃዱ ባይኾን ግልጽ ባልነበረ ምክንያት ዐውደ ርእዩ መታገዱ ሲሰማ ብዙ ምእመናን ተደናገጡ፡፡

የማኅበሩ ሥራ አመራር አባላትም፡- አይዟችሁ አትደንግጡ፤ ኹሉም በጊዜው ይኾናል፡፡ እግዚአብሔር በፈቀደበት ጊዜ ዐውደ ርእዩን እናሳያችኋለን፡፡ እስከዚያው ድረስ ግን በትዕግሥት ኾነን እንጠባበቅ፤ ወዘተ እያሉ ዐውደ ርእዩን በጉጉት ሲጠባበቁ የነበሩትን ምእመናን እያጽናኑ ከሚመለከታው አካላት ጋር ውይታቸውን ቀጠሉ፡፡

እግዚአብሔር ሥራውን የሚሠራበት ጊዜ ሲደርስ በእግዚአብሔር ቸርነት፣ በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት፣ በቅዱሳን ተራዳኢነት፣ በአባቶችና በእናቶች ጸሎት የማኅበሩና የተባባሪዎቹ ጥረት ተሳክቶ ዐውደ ርእዩ የሚታይበት ቀን ደርሶ እነሆ ከግንቦት 17 ቀን 2008 ዓ.ም ጀምሮ በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል ለተመልካቾቹ ይፋ ኾነ፡፡

መስቀል ዐደባባይን በማቋረጥ ከሰሜን ወደ ምዕራብ አቅጣጫ ከፍ ብሎ ወደሚገኘው ቅፅር ግቢ ውስጥ ሲገሰግሱ የኢትዮጵያውያንን ባህል ገላጭ የኾነውንና ጠቢባኑ የተካኑበትን በረጅሙ ቆሞ ከርቀት የሚታየውን በኅብረ ቀለማት ያጌጠውን መሶብ ያገኛሉ፡፡

ይህንን መሶብ አለፍ እንዳሉ በግዙፉ መግቢያ በር ላይ አምስተኛው ዙር የማኅበረ ቅዱሳን ዐውደ ርእይ በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል፣ ከግንቦት 17-22 ቀን 2008 ዓ.ም የሚሉ ማስታዎቂያዎች በረጅም ብራና ቁልቁልና አግድም ተለጥፈው ይነበባሉ፡፡

ከታች ደግሞ የጸጥታ ባለሙያዎች ተመልካቾችን በጥንቃቄ እየፈተሹ ወደ ኤግዚብሽን ማዕከሉ ቅፅር እንዲገቡ ያደርጋሉ፡፡ የዐውደ ርእዩ ታዳሚዎችም በሩ ውስጥ የተመደቡትን የቲኬት ሽያጭ አስተባባሪዎች ፈቃድ ካገኙ በኋላ ወደ አዳራሾቹ ጥቂት እንደተጓዙ ከአስፋልቱ በስተቀኝ በኩል ተንጣሎ የሚታየውን ቍጥር አንድ አዳራሽን ያገኛሉ፡፡ ይህ አዳራሽ በቍጥር የመጀመሪያው ይሁን እንጂ በዐውደ ርእዩ ትዕይንቶች ግን የመጨረሻው ነው፡፡

በአስተባባሪዎች መሪነት ወደ ሰሜን ምዕራብ አቅጣጫ ጥቂት ተጉዘው ጊዜያዊ የእንግዶች ማረፊያ ድንኳን ውስጥ ቁጭ ብለው በድምፅና በምስል የታገዙ ልዩ ልዩ መንፈሳውያን መረጃዎችን ሲከታተሉ ከቆዩ በኋላ በተራ ቅደም ተከተላቸው መሠረት ወደ ትዕይንቱ አዳራሾች ያመራሉ፡፡

የኤግዚብሽን ማዕከሉ በስተሰሜን በኩልም ተጨማሪ የመግቢያ በር ያለው ሲኾን፣ እንደዋናው በር ኹሉ የመግቢያ ቅድመ ኹኔታዎችን ካሟሉ በኋላ ወደ ደቡብ አቅጣጫ ሲያመሩ በዋናው በር ከገቡ ታዳሚዎች ጋር በአንድ ድንኳን ውስጥ አብረው እንዲቆዩ ይደረጉና ወደ ትዕይንቶች ይገሰግሳሉ፡፡

ይህ መንፈሳዊ ዐውደ ርእይ በአባቶች ጸሎት ከተከፈተበት ዕለት ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ በርካታ ምእመናን እየተመለከቱት ሲኾን፣ የምእመናኑ ቍጥርም ከዕለት ወደ ዕለት እየጨመረ ነው፡፡

የዐውደ ርእዩ አዘጋጆችና አስተባባሪዎቹ ምእመናኑ ረጅም ሰዓት በመቆም እንዳይጉላሉ በማሰብ የሚቻላቸውን ኹሉ ጥረት በማድረግ ላይ ይገኛሉ፡፡ ስለዚህም ከኤግዚብሽን ማዕከሉ አዳራሾች በተጨማሪ ሰፋፊ ድንኳኖችን በማዘጋጀት ተጨማሪ መመልከቻ ቦታዎችን አመቻችተዋል፡፡

ትዕይንታተ ዐውደ ርእይ

ዐውደ ርእዩ በሦስት መንገድ ይጎበኛል፤ ይኸውም በገላጮች ማብራሪያ፣ በባነሮች (ብራናዎች) ላይ በተቀመጡ ጽሑፎችና መረጃዎች እንደዚሁም በድምፅ ወምስል በመታገዝ ነው፡፡ የዐውደ ርእዩ ዐበይት አርእስትም አራት ሲኾኑ እነዚህም፡-

የመጀመሪያው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መሠረተ እምነት፤ ሁለተኛው የቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ ተልዕኮ፤ ሦስተኛው የቤተ ክርስቲያን ተጋድሎ፤ አራተኛው ደግሞ ምን እናድርግ የሚሉ ናቸው፡፡ የእያንዳንዳቸውን ጭብጥ ለማስገንዘብ ያህል የአርእስቱን ዐሳብ በአጭሩ እንመልከት፤

ትዕይንት አንድ፡- የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መሠረተ እምነት

ይህ ትዕይንት ሀልዎተ እግዚአብሔር፣ ነገረ ድኅነት፣ ነገረ ማርያም፣ ነገረ ቅዱሳን እና ነገረ ቤተ ክርስቲያን የተካተቱበት ክፍል ነው፡፡ ሀልዎተ እግዚአብሔር በሚለው ርእስ እግዚአብሔር አምላክ በጊዜና በቦታ የማይወሰን፣ መጀመሪያና መጨረሻ የሌለው፣ የፍጥረታት ኹሉ አስገኝ፣ ከመሥፈርትና ከአመለካከት ውጪ፣ እርሱ በገለጠው መጠን ብቻ የሚታወቅ እንጂ ባሕርዩ ተመርምሮ ሊደረስበት እንደማይቻል እንደዚሁም መልዕልተ ኵሉ (የኹሉ የበላይ) ኾኖ ሳለ በፈቃዱ የትሕትና ሥራ መሥራቱን ያስረዳል፡፡

ነገረ ድኅነት ደግሞ በአዳምና በሔዋን ምክንያት የዘለዓለም ሞት ተፈርዶበት የነበረው የሰው ልጅ ከሦስቱ አካላት አንዱ በኾነው በጌታችን በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሕማማተ መስቀልና ሞት የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ መቻሉን፤ ንደዚሁም እምነት፣ ምግባር እና ምሥጢራተ በቤተ ክርስቲያንን መፈጸም የሰው ልጅ ለመዳን የሚያስፈልጉት ነገሮች መኾናቸው በዚህ ርእስ ሥር ተካቷል፡፡

ትዕይንት ሁለት፡- የቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ ተልዕኮ

በዚህ ትዕይንት የሐዋርያነትና የሐዋርያዊ አገልግሎት ትርጕም፣ ዓላማና አመሠራረትን ጨምሮ ስብከተ ወንጌል አንዴት እንደተስፋፋና እስከ ዛሬ ድረስ በቤተ ክርስቲያን ላይ የደረሱ ፈተናዎችን እንደዚሁም መልካም አጋጣሚዎችን በማካከተት ልዩ ልዩ መረጃዎችና ትምህርቶቸ ቀርበውበታል፡፡

ትዕይንት ሦስት፡- የቤተ ክርስቲያን ተጋድሎ

ይህ ትዕይንት ቤተ ክርስቲያን ወንጌልን ለማስፋፋት ያሳለፈችውን ተጋድሎ፣ የመናፍቃንን ተፅዕኖና የሰማዕታትን ታሪክ፣ የተዋሕዶ ሃይማኖትን አስተምህሮ ለማስጠበቅ የተደረጉ ልዩ ልዩ ዓለም ዓቀፍና አገር ዓቀፍ ጉባኤያትን በዝርዝር ይዟል፡፡

ትዕይንት አራት፡- ምን እናድርግ?

ይህ ትዕይንት ደግሞ ምእመናን በዐውደ ርእዩ ከተመለከቷቸውና ከሰሟቸው እውነታዎች በመነሣት የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ከመጠበቅና ድርሻን ከማወቅ አኳያ ልዩ ልዩ ችግሮችን ለመቅረፍ ወደፊት ምን ማድረግ እንደሚጠበቅባቸው የሚያስረዱ መረጃዎችን አካቷል፡፡

ዐውደ ርእዩ ከነዚህ ዐበይት ትዕይንቶች በተጨማሪ የሕፃናት ትዕይንትም የተካተተበት ሲኾን፣ በዚህ ትዕይንት ለሕፃናት አእምሮ የሚመጥኑ መንፈሳውያን ትምህርቶች ተዘጋጅተውበታል፡፡ ሕፃናቱም ክፍሉ ውስጥ እየዘመሩ ይማራሉ፤ ይደሰታሉ፡፡

ከሁሉም በተለየ መንገድ ደግም የሁሉም ገባኤያት (የንባብ፣ የዜማ/የድጓ፣ የቅዳሴ፣ የቅኔ፣ የአቋቋም፣ የመጻሕፍትና የአቡሻሕር ጉባኤ ቤቶች) ሊቃውንት (መምህራን) ደቀ መዛሙርታቸውን ሲያስተምሩ እስከ ጎጆዎቻቸውና እስከሚጠቀሙባቸው ዕቃዎች ድረስ በተግባር ይታያሉ፡፡ የብራና መጻሕፍት አዘገጃጀትም በባለሙያ አባቶች ይብራራል፡፡

የማኅበረ ቀዱሳንን ልዩ ልዩ ክፍሎች፣ እንደዚሁም የጽርሐ ጽዮንና የደጆችሽ አይዘጉ መንፈሳውያን ማኅበራት አገልግሎት የሚቃኝባቸው ክፍሎችም የትዕይንቱ አካላት ናቸው፡፡ በማኅበሩ የሚዘጋጁ ንዋያተ ቅድሳትና መጻሕፍትም በሽያጭና በዕጣ መልክ ቀርበዋል፡፡

ማኅበረ ጽዮን የጉዞ ማኅበር፣ መቄዶንያ የአረጋውያንና የአእምሮ ሕሙማን መርጃ ማዕከል፣ ዮድ አቢሲንያ አስጎብኚና የጉዞ ወኪል ስለሚሰጧቸው ተግባራት የሚገልጹባቸው ክፍሎችም ተካተዋል፡፡

ትዕይንቶቹን ተመልክተው የሚወጡ ምእመናንም ኾኑ የሌሎች እምነት ተከታዮች ለሚያነሷቸው ጥያቄዎች ምላሽ የሚሰጡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን መውጫው በር ላይ ተሠይመዋል፡፡

የዐውደ ርእዩ ታዳሚዎች ጉብኝቱን ጨርሰው ሲወጡ ደግሞ የተሰማቸውን ስሜት ወይም ደግሞ ቅሬታ የሚያሰፍሩባቸው የአስተያየት መስጫ መዛግብት በብዛት ተደርድረዋል፤ ጎብኝዎቹም ስሜታቸውን እየጻፉ ወደየመጡበት ይመለሳሉ፡፡

ከዐውደ ርእዩ ትዕይንቶች ጎን ለጎንም ከግንቦት 17 ቀን 2008 ጀምሮ የአብነት ትምህርቶችን የተመለከቱ ጥናቶችና መንፈሳውያን ተውኔቶች እንደዚሁም መዝሙራት ከቀኑ 11፡00 እስከ ምሽት ድረስ ለጎብኝዎቹ በመቅረብ ላይ ይገኛሉ፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ለአምስተኛ ጊዜ ያዘጋጀው ይህ ዐውደ ርእይ መታየት ከጀመረ እነሆ ዛሬ አምስተኛውን ቀን ያስቈጠረ ሲኾን፣ እጅግ በሚማርክ ኹኔታ በአባቶች ካህናትና በምእመናን ብቻ ሳይኾን በሌሎች ሰዎችም እየተጎበኘ ይገኛል፡፡

ትናንትናና ዛሬም በርካታ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት በዐውደ ርእዩ ተገኝተው አባታዊ ቡራኬ ሰጥተዋል፤ ማኅበሩ እየሠራ ያለውን ተግባር በማድነቅም ስሜታቸውን መዝገብ ላይ አስፍረዋል፡፡

ለዐውደ ርእዩ ድምቀት ከሰጡ ክሥተቶች መካከልም የሰንበት ት/ቤት ዘማርያን የመዝሙር ልብስ ለብሰው እየዘመሩ፤ እንደዚሁም በዛሬው ዕለት (ግንቦት 21 ቀን 2008 ዓ.ም) ጋብቻቸውን የፈጸሙ ጥንዶች ከአጃቢዎቻቸው ጋር በመኾን በዐውደ ርእዩ መታደማቸው ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡

ዐውደ ርእዩ ከተከፈተበት ቀን ጀምሮ በአስተያየት መስጫ መዛግብቱ ላይ የሰፈሩትን አስተያየቶች ስናነብና ቃለ መጠይቅ ስናደርግ ብዙ ምእመናን በዐውደ ርእዩ ራሳቸውን እንዳዩበትና ስለሃይማኖታቸው በቂ ግንዛቤ እንዳስጨበጣቸው እንደዚሁም የድርሻቸውን ለመወጣት እንዳነሣሣቸው ተረድተናል፡፡

በተጨማሪም ዐውደ ርእዩ በዐዲስ አበባ ብቻ ሳይኾን በየአገሩ ቢታይ፣ ትዕይንቶቹ በብሮሸርና በሲዲ መልክ ቢሠራጩ፣ ከጠቅላይ ቤተ ክህነትና ከሰንበት ት/ቤት ወጣቶች ጋር በጋራ በመኾን ማቅረብ ቢቻል መልካም ነው የሚሉና የመሳሰሉ አስተያየቶች ተሰጥተዋል፡፡

በአንጻሩ በትዕይንቶቹ ገላጮችና በምስል ወድምፅ ዝግጅቶች መካከል የድምፅ መጋጨት እንዳይኖር ጥንቃቄ ቢደረግ፤ ግቢው ውስጥ በማኅበሩ የተዘጋጁ ምግቦችና መጠጦች ለሽያጭ ቢቀርቡ፤ ትዕይንቶቹ ሰፊ ጊዜ ተሰጥቷቸው በስፋት ቢተነተኑ፤ አዳራሾቹ ውስጥ ረጅም ሰዓት መቆየት ባይኖር፤ ወዘተ የመሰሉ በርካታ አስተያየቶችንም ከአንዳንድ ጎብኝዎች ለመረዳት ችለናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የቅዱስ ሲኖዶስን ጉባኤ መጀመር አስመልክቶ ከቅዱስ ፓትርያሪኩ የተሰጠ መግለጫ

ግንቦት ፲፯ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

የተወደዳችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች፣ እንደሚታወቀው የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ በዛሬው ዕለት ተጀምሯል፤ ቅዱስ ፓትርያሪኩ ጠዋት ለቅዱስ ሲኖዶስ አባላትና ለጋዜጠኞች የሰጡትን ሙሉ መግለጫ እንደሚከተለው አቅርበነዋል፤

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡

ወዓዲ እብለክሙ ለእመ ኀብሩ ክልኤቱ አው ሠለስቱ እምኔክሙ በውስተ ምድር በእንተ ኵሉ ግብር ዘሰአሉ ይትገበር ሎሙ በኀበ አቡየ ዘበሰማያት እስመ ኀበ ሀለዉ ክልኤቱ ወሠለስቱ ጉቡአን በስምየ ህየ እሄሉ አነ ማእከሎሙ፤ ዳግመኛም ከእናንተ ሁለቱ ወየም ሦስቱ በምድር ላይ ስለሚለምኑት ሥራ ሁሉ ቢተባበሩ፣ በሰማያዊ አባቴ ዘንድ ይደረግላቸዋል፤ ሁለቱ ወይም ሦስቱ በስሜ ተሰብስበው ካሉበት፣ እኔ ከዚያ በመካከላቸው እገኛለሁና /ማቴ.፲፰፥፲፱-፳/፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፤

ከጌታችን፣ ከአምላካችንና ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ የተሰጠንን ዓቢይ ተልእኮ ወይም ሐዋርያዊ አገልግሎት በየተሠማራንበት ሀገረ ስብከት ስናከናውን ቆይተን፣ በዓለ ትንሣኤውን ካከበርን በኋላ፣ በቀኖና ሐዋርያት ድንጋጌ መሠት፣ ስለ ቤተ ክርስቲያናችን ጉዳዮች ለመነጋገር በዚህ በረክበ ካህናት ዓመታዊ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ አንድ ላይ ስለሰበሰብን፣ አምላካችን እግዚአብሔርን እናመሰግነዋለን፡፡

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በማይታበል ቃሉ እንዳስተማረን፣ ለቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ የገባው ቃል ኪዳን አለ፤ እርሱም ከቅዱሳን ሐዋርያት ጋር የተፈጸመ ጽኑ ቃል ኪዳን ነው፡፡ ቃል ኪዳኑም፡- ሁለቱ ወይም ሦስቱ በስሜ በተሰበሰቡበት፣ እኔ ከዚያ በመካከለቸው እገኛለሁ ይላል፡፡ በሁሉም ዘንድ እንደሚታወቀው፣ ቃል ኪዳን በሁለት ወገኖች መካከል የሚፈጸምና ለቃል ኪዳኑ መከበር የሁለቱንም የቃል ኪዳን አካላት ኃላፊነት በግልጽ የሚያስቀምጥ ነው፤በዚህ ሁኔታ እግዚአብሔር ከጥንት ጀምሮ ከቅዱሳን አበው ጋር ቃል ኪዳን መሥርቶ እንደነበረ በቅዱስ መጽሐፍ በየቦታው ተጽፎ እናገኛለን፡፡

ይሁንና በዘመነ ሐዲስ ጌታችን ቃል ከገባባቸው ዓበይት ነገሮች አንዱ፣ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ነው፡፡ በዚህ ቃል ኪዳን ውስጥ ቅዱስ ሲኖዶስ በስመ ኢየሱስ ክርስቶስ እንዲሰበሰብ ሓላፊነት ተሰጥቶታል፡፡ ጌታችንም በስሙ በሚደረግ ጉባኤ እንደሚገኝ ቃል ገብቶአል፡፡

በመሆኑም የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ፣ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በርእሰ መንበርነት፣ ቅዱስ ፓትርያርክ በመሪነት፣ ሊቃነ ጳጳሳት በአባልነት የሚገኙበት ዓቢይ ጉባኤ ነው፡፡ ቅዱስ ወይም ልዩ ጉባኤ የሚያሰኘውም ቅሉ፣ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በርእሰ መንበርነት የሚገኝበት በመሆኑ ነው፡፡ ይህ ጉባኤ ጌታችን እስከ ዓለም ፈጻሜ ድረስ እንደማይለየው ሲገልጽ፡- ወናሁ አነ እሄሉ ምስሌክሙ እስከ ኅልቀተ ዓለም፤ እነሆ እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ እኔ ከናንተ ጋር ነኝ ብሎ በቃሉ አረጋጦአል /ማቴ.፳፰፥፳/፡፡

እንግዲህ በየጊዜው ስመ እግዚአብሔርን ጠርተን በስሙ፣ ስለስሙ ብለን የምናካሂደው ቅዱስ ጉባኤ ወይም ቅዱስ ሲኖዶስ ይህን ያህል ታላቅ ክቡርና ጽኑ የሆነ አምላካዊ ቃል ኪዳን ያለው እንደመሆኑ መጠን፣ ለደረጃው በሚመጥን ክብርና ልዕልና መካሄድ ይኖርበታል፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፤

ጌታችን፣ አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያንን በአደራነት ያስረከበ ለዚህ ጉባኤ እንደሆነ በውል የሚታወቅ ነው፡፡

ይህ ቅዱስ ጉባኤ የእግዚአብሔር መንግሥት ወኪል እንደመሆኑ መጠን ድንበር የለውም፤ ምክንያቱም የእግዚአብሔር መንግሥት ድንበር የለውምና፡፡ ይህ ጉባኤ ገደብ የለሽ መንፈሳዊ ሥልጣን ከሕያው አምላክ ሲሰጠው፣ ወደ ዓለም ሁሉ ሂዱ፤ ወንጌልንም ለፍጥረት ሁሉ ስበኩ ከሚል ትእዛዝ ጋር መታዘዙ የቅዱስ ሲኖዶስ መንፈሳዊ ሥልጣን ድንበር የማይገድበው መሆኑን በግልጽ ያሳያል /ማር.፲፮፥፲፭/፡፡

በመሆኑም የዚህ ቅዱስ ጉባኤ ሥራና ሓላፊነት ዓለም አቀፋዊ ይዘት ያለው መሆኑ ሊሠመርበት ይገባል፡፡ ይህም በመሆኑ ነው ዛሬ ቤተ ክርስቲያናችን በሁሉም ክፍላተ ዓለም አብያተ ክርስቲያናትን ከፍታ ሐዋርያዊ ተልእኮዋን በማካሄድ ላይ የምትገኘው፡፡

ይሁንና አሁን የምንገኝበት የሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን ወቅት፣ የሴኩላሪዝም አስተሳሰብ ያየለበት፤ የዓለም ሉላዊነት የበረታበት፣ የጽንፈኝነትና የሽብርተኝነት መንፈስ የተስፋፋበት፣ እነዚህ ሁሉ በየፊናቸው ተሰልፈው በሃይማኖት ላይ ከባድ ተጽዕኖ የፈጠሩበት ዘመን ነው፡፡ ዓለም በዚህ ሥጋዊ ፍልስፍና እና ቁሳዊ አምሮት ቤተ ክርስቲያንን ለመውጋት ስትዘጋጅ እኛ የክርስቶስ ወኪሎች እንዲሁ ዝም ብለን የምናይበት ኅሊና ሊኖረን አይችልም፡፡

ቀደምት አበው እሾህን በእሾህ ብለው እንደተናገሩት፣ የዓለምን ጥበብ በክርስቶስ ጥበብ ለመቋቋም፣ በዓለም እየሆነ ያለውን ነገር ሁሉ መከታተልና ማወቅ፣ ለወደፊትም ሊያስከትለው የሚችለውን ሃይማኖታዊ፣ ማኅበራዊ፣ ሰብአዊና ባህላዊ ቀውስ አስቀድሞ በመተንበይ፣ ሕዝቡን በእግዚአብሔር ቃል ኃይል መጠበቅና መንከባከብ ከእኛ ይጠበቃል፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፤

በሃይማኖት ዙሪያ ያንዣበቡ እነዚህ ዓለም አቀፍ ተፅዕኖዎች እጅግ አስጊ ቢሆኑም፣ እነርሱን ለመከላከል ብሎም ለመቀልበስ አሁንም ቢሆን ጊዜው አልመሸም፡፡ በተለይም በሀገራችን ያለው ሕዝብ፣ አሁንም ምርጫው እግዚአብሔርንና የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን እንደሆነ በተጨባጭ የምናውቀው ሐቅ ነው፡፡ ይህንን ሕዝብ በሚገባ ማገልገል ከተቻለ፣ ችግሩን በሚገባ መቋቋም ይቻላል፡፡

ስለሆነም ሕዝበ ክርስቲያኑን በአግባቡ ለማገልገልና ለመጠበቅ፣ ከሁሉም በፊት የሕዝቡን ጥያቄ ማወቅ ያስፈልጋል፤ ቀጥሎም ለጥያቄው ተገቢ የሆነ መልስ በመስጠት ፍጹም መግባባት መፍጠር ይገባል፡፡ ሕዝበ ክርስቲያኑ ከሃይማኖት መሪዎችና ከአገልጋይ ካህናት የሚጠብቀውን ሁለንተናዊ አገልግሎት በሚገባ ካገኘና በሃይማኖቱ እንዲኮራ የሚያስችል ሁኔታ ከተመቻቸለት፣ ለተጠቀሱ ዓለም ዓቀፍ ተፅዕኖዎች ተንበርካኪ አይሆንም፡፡ ስለሆነም የኛው የጥበቃ ስልት መቀየስ ያለበት በዚሁ መንፈስ አቅጣጫ ነው፡፡

ሕዝበ ክርስቲያኑ በአሁኑ ጊዜ የሚጠይቃቸው ብዙ ነገሮች አሉ፤

ሕዝቡ፣ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎትና ለሃይማኖት መጠበቂያ ብሎ በእምነት የሚለግሰው ገንዘብና ንብረት ከምዝበራ ተጠብቆ ለታለመለት ዓላማ ብቻ እንዲውል ይፈልጋል፤

በቤተ ክርስቲያን ውስጥ መልካም አስተዳደር ሰፍኖ አድልዎ፣ ጭቅጭቅ፣ ንትርክ፣ መለያየት በአጠቃላይ ከሃይማኖቱ መርሕ ጋር የማይጣጣም ኋላ ቀር አሠራርና አስተሳሰብ ተወግዶ የተስተካከለ ሥርዓትን ማየት ይፈልጋል፤

ስለሃይማኖት ክብርና ህልውና ከልብ የሚቆረቆሩ፣ መልካም የሆነ ሥነ ምግባርና የተስተካከለ ሰብእና ያላቸው እንደዚሁም በኑሮአቸው ሁሉ ለሕዝበ ክርስቲያኑ እንደ ሞዴል የሚጠቀሱ ውሉደ ክህነትና ሠራተኞች እንዲመሩት ይፈልጋል፤

ሕዝቡ ቤተ ክርስቲያን በሁሉም መስክ ጠንካራ ዓቅምን ገንብታ እንደዚሁም ለሕዝበ ክርስቲያኑ መንፈሳዊና ማኅበራዊ ችግር ደራሽና አለሁላችሁ ባይ ኾና ማየት እንደሚፈልግ ከሚያነሣው ጥያቄ ማወቅ ይቻላል፡፡

ብፁዓን ሊቃ ጳጳሳት፣ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፤

የእኛ ተልእኮ እግዚአብሔርንና ሕዝብን ማገልገል ከሆነ፣ የሕዝቡ ጥያቄም ከሞላ ጎደል የሚታወቅ ከሆነ፣ በተሰጠን አደራና ሓላፊነት መሠረት የሕዝበ ክርስቲያኑን ጥያቄ በጽሞና አዳምጠንና ተቀብለን፣ በቅዱስ መጽሐፍ አስተምህሮ፣ በቀኖና ቤተ ክርስቲያን ድንጋጌና ባሉን የቤተ ክርስቲያን ሕጎች ማእከልነት፣ ጥያቄውን የማስተናገድ ክርስቶሳዊ ግዴታ አለብን፡፡

ከሕግ የወጣ የሥራ አፈጻጸም ሲኖርም፣ ጥብቅ ክትትልና ቁጥጥር በማድረግ በወቅቱ ማረም ያስፈልጋል፡፡

ቅዱስ ሲኖዶስ የቤተ ክርስቱያናችን የመጨረሻ ውሳኔ ሰጭ አካል እንደመሆኑ መጠን፣ የቤተ ክርስቲያናችንን መልካም አስተዳደር ለማስፈን የሚያስችሉ ሕጎችን፣ ልዩ ልዩ ደንቦችን፣ መመሪያዎችን፣ ፖሊሲዎችንና ስትራቴጂዎችን በማዘጋጀትና በማጽደቅ፣ እንደዚሁም በአፈጻጸማቸው ጥብቅ ክትትልና ቁጥጥር በማድረግ፣ ሕዝበ ክርስቲያኑን እሰየው የሚያሰኝ አሠራር ማረጋገጥ አለብን፡፡ ይኸ ሲሆን ብቻ ነው ሕዝቡን ከቁሳዊው ዓለም ማዕበል መታደግ የምንችለው፡፡

በመጨረሻም

ይህ የተቀደሰ ክርስቶሳዊና ሐዋርያዊ ጉባኤ ከልዩ ልዩ የቤተ ክርስቲያናችን አመራር አካላትና ከጉባኤው የሚቀርቡትን ሃይማኖታዊ ሀገራዊ ጉዳዮችን በጥልቀት በመፈተሽና በመመርመር እንደዚሁም ሕጋዊና ቀኖናዊ መፍትሔ በማስቀመጥ የተሳካ ውጤት ያስመዘግብ ዘንድ ወደ እግዚአብሔር እየጸለይንና ከልብ እየተመኘን የ፳፻፰ ዓ.ም የረክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ዛሬ መከፈቱን እናበሥራለን፡፡

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ፤ ይቀድስ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፤

አሜን፡፡

አባ ማትያስ ቀዳማዊ

ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም

ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

ግንቦት ፲፯ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ፡፡