ሠለስቱ ደቂቅን ከእሳት ያዳናቸው መልአክ ማን ነው? – ክፍል ሁለት

በዲያቆን ብርሃኑ አድማስ

ታኅሣሥ ፳፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

እንድንበላቸውና እንዳንበላቸው የታዘዝናቸው እንስሳት ከላይ በተገለጸው መንገድ እኛን የሚወክሉ መኾንና አለመኾናቸውን የሚያረጋግጥ የቅዱሳት መጻሕፍት ምስክርነት ወይም የሐዋርያዊው ትምህርት ትውፊት አለ ወይ? ከተባለ አዎን፤ በእርግጥ አለ፡፡ ሰፊውና ዋነኛው ምስክርም ቅዱስ ጴጥሮስ ያየው ራእይ ነው፡፡

በሐዋርያት ሥራ ‹‹… ተርቦም ሊበላ ወደደ፤ ሲያዘጋጁለት ሳሉም ተመስጦ መጣበት፡፡ ሰማይም ተከፍቶ በአራት ማዕዘን የተያዘ ታላቅ ሸማ የሚመስል ዕቃ ወደ ምድር ሲወርድ አየ፤ በዚያውም አራት እግር ያላቸው ዅሉ አራዊት፣ በምድርም የሚንቀሳቀሱ የሰማይ ወፎችም ነበሩበት፡፡ጴጥሮስ ሆይ፣ ተነሣና አርደህ ብላ!› የሚልም ድምፅ ወደ እርሱ መጣ፡፡ ጴጥሮስ ግን ‹ጌታ ሆይ አይሆንም፤ አንዳች ርኩስ የሚያስጸይፍም ከቶ በልቼ አላውቅምና› አለ፡፡  ደግሞም ሁለተኛ ‹እግዚአብሔር ያነጻውን አንተ አታርክሰው› የሚል ድምፅ ወደ እርሱ መጣ፡፡ ይህም ሦስት ጊዜ ኾነ፡፡ ወዲያውም ዕቃው ወደ ሰማይ ተወሰደ፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈው /ሐዋ.፲፥፲-፲፮/፣ ቅዱስ ጴጥሮስ ይህን ራእይ ደጋግሞ ካየ በኋላ ራእዩ በቀጥታ ምግብ ሳይኾን ምሥጢራዊ መልእክት እንዳለው ተረድቶ ‹‹ትርጕሙ ምን ይኾን?›› እያለ ሲያስብ ነበር፡፡

በኋላም መንፈስ ቅዱስ ምሥጢሩን ገለጸለት፤ ‹‹… ጴጥሮስም ስለ ራእዩ ሲያወጣ ሲያወርድ ሳለ መንፈስ እነሆ ሦስት ሰዎች ይፈልጉሃል፤ ተነሥተህ ውረድ፡፡ እኔም ልኬአቸዋለሁና ሳትጠራጠር ከእነርሱ ጋር ሒድ አለው፤›› እንዲል /ቍ. ፲፱-፳/፡፡ ከታዘዘው ቦታ ከደረሰ በኋላም ‹‹አይሁዳዊ ሰው ከሌላ ወገን ጋር ይተባበር ወይም ይቃረብ ዘንድ እንዳልተፈቀደ እናንተ ታውቃላችሁ፤ ለእኔ ግን እግዚአብሔር ማንንም ሰው ‹ርኩስና የሚያስጸይፍ ነው› እንዳልል አሳየኝ፤›› በማለት ምስክርነቱን አስቀደመ /ቍ. ፳፯/፡፡ በዚህ ራእይ ያያቸው የማይበሉ እንስሳትም ምሳሌነታቸው ከእምነት ውጪ ላሉ ሰዎች እንደ ኾነ አረጋገጠ፡፡

ጌታችንም በዘመነ ሥጋዌው በሚያስተምርበት ጊዜ ‹‹… መንግሥተ ሰማያት ወደ ባሕር የተጣለች ከዅሉም ዓይነት የሰበሰበች መረብን ትመስላለች፤ በሞላችም ጊዜ ወደ ወደቡ አወጧት፡፡ ተቀምጠውም መልካሙን ለቅመው በዕቃዎች ውስጥ አከማቹ፤ ክፉውን ግን ወደ ውጪ ጣሉት፤›› በማለት /ማቴ.፲፫፥፵፯-፵፰/፣ መረብ የተባለችው ቤተ ክርሰቲያን ዅሉንም እንደምታጠምድ (ወደ እርሷ እንደምታቀርብ)፤ የዓሣዎቹ ሐዋርያትን ትምህርታቸውን ንቀው ከቤተ ክርስቲያን ወጥተው የሚወድቁት ደግሞ መናፍቃንና ኀጥአንን እንደሚወክሉ በምሳሌ አስተምሮናል፡፡

ለመሥዋዕት የሚቀርቡት እንስሳትም የሰማዕታትና የቅዱሳን ምሳሌዎች መኾናቸውን ቅዱስ መጽሐፍ ያስረዳናል፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት ‹‹አቤቱ ስለ ምን ለዘወትር ጣልኸኝ? በማሰማርያህ በጎች ላይስ ቍጣህን ስለ ምን ተቈጣህ?›› በሚለው መዝሙሩ መምለክያነ እግዚአብሔር እስራኤልን በጎች ብሎ ጠርቷቸዋል /መዝ.፸፬፥፩/፡፡  ‹‹እንደ በጎች ሊበሉን ሰጠኸን፤ ወደ አሕዛብም በተንኸን፤›› ዳግመኛም ‹‹ስለ አንተ ዅልጊዜም ተገድለናል፡፡ እንደሚታረዱም በጎች ኾነናል›› በማለት ሰማዕትነታቸውና ተጋድሏቸው እንደ መሥዋዕት በጎች እንደሚያስቈጥራቸው ተናግሯል /መዝ.፵፬፥፲፩-፳፪/፡፡  ይህ ቃል በእርግጥ ስለ ሰማዕታት የተነገረ መኾኑንም ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹ስለ አንተ ቀኑን ዅሉ እንገደላለን፤ እንደሚታረዱ በጎችም ተቈጠርን፤›› በማለት አረጋግጦልናል /ሮሜ.፰፥፴፮/፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ የደረሰበትን መከራና ሰማዕትነቱን ሲገልጽ ‹‹በመሥዋዕት እንደሚደረግ የእኔ ሕይወት ይሠዋልና፤ የምሔድበትም ጊዜ ደርሷል፤›› በማለት ሕይወቱን በመሥዋዕት መስሎ መናገሩም /፪ኛጢሞ.፬፥፮/፣ ጥንቱንም እነዚህ የመሥዋዕት እንስሳት የቅዱሳን፣ የንጹሐን ምእመናን፤ ርኩሳን የተባሉት ደግሞ የማያምኑትና የመናፍቃን ምሳሌዎች መኾናቸውን አመላካች ነው፡፡ ጌታችንም በነቢዩ በሕዝቅኤል ላይ አድሮ ‹‹‹እናንተም በጎቼ፣ የማሰማርያዬ በጎች ሰዎች ናችሁ፤ እኔም አምላካችሁ ነኝ› ይላል ጌታ እግዚአብሔር፤›› በማለት በተናገረው ቃል /ሕዝ.፴፬፥፴፩/ እስራኤልን ‹‹በጎቼ›› ብሏቸዋል፡፡ ነቢያትም ዅሉ ይህን ቃል ደጋግመው ተናግረውታል፡፡ ጌታችንም በዘመነ ሥጋዌው ቃሉን አጽድቆታል፡፡ በመጨረሻው ዕለትም ‹‹በዚያን ጊዜ ኢየሱስ፦ በዚች ሌሊት ሁላችሁ በእኔ ትሰናከላላችሁ፡፡ ‹እረኛውን እመታለሁ፤ የመንጋውም በጎች ይበተናሉ› የሚል ተጽፎአልና፤›› /ማቴ.፳፮፥፴፩/ ያላቸው ቅዱሳኑ፣ ንጹሐኑ የመሥዋዕቱ እንስሳት የሚያመሰኩትና ቆንጥጦ ለመርገጥ የሚያስችል ስንጥቅ ሰኮና ያላቸው እነርሱ በመኾናቸው ነው፡፡

ስለዚህ በዘመነ ኦሪት ከሁለቱም ወገን የሚመደቡ እንስሳትን የሚያርዱና የሚበሉ ሰዎች የነበሩ ቢኾንም እግዚአብሔርና የእርሱ የኾኑት የሚቀበሉት ግን ከንጹሐን ወገን የኾኑትን እንስሳት ብቻ ነበር፡፡ ይህም ምሳሌ ስለ ኾነ ዛሬም ከሁለቱም ወገን የሚመደብ አለ፤ እግዚአብሔርና የእግዚአብሔር የኾኑት የሚቀበሉትም በንጹሐን እንስሳት ከተመሰሉት ከሐዋርያት፣ ከሰማዕታት፣ ከቅዱሳን ሊቃውንትና ከእውነተኞች መምህራን የሚገኘውን ትምህርት ብቻ ነው፡፡ ቀደም ብለን እንደ ገለጽነው እነዚህ ቅዱሳን በበግና በመሳሰሉት የተመሰሉት ሰኮናቸው የተሰነጠቀ እንስሳት በትክክል መሬትን ጨብጦ ወይም ቆንጥጦ መርገጥ እንደሚችሉት እንደዚሁ ሃይማኖታቸውን በሥራ ገልጠው ከእነርሱ የሚጠበቀውን መሥዋዕትነት ወይም ሰማዕትነት በገቢር ገልጸው የሚኖሩ በመኾናቸው ነው፡፡ በባሕር ውስጥ በሚኖረው ቅርፊትና ክንፍ ባለው ዓሣ የተመሰሉትም በዚህ እንደ ባሕር በሚነዋወጥ ዓለም ውስጥ እየኖሩ ወደ ከፍተኛው ጸጋና ክብር ብቻ ሳይኾን ወደ ላይኛው መለኮታዊ ምሥጢር ብቅ የሚሉበት ክንፈ ጸጋ፣ የዚህን ዓለም አለማመን፣ ክሕደትና ኑፋቄ ድል የሚነሡበት በቅርፊት የተመሰለ የእምነት ጋሻና ጦር ስላላቸው ነው፡፡

እኛንም ‹‹በዅሉም ላይ ጨምራችሁ የሚንበለበሉትን የክፉውን ፍላጻዎች ሁሉ ልታጠፉ የምትችሉበትን የእምነትን ጋሻ አንሡ፤›› ሲሉ አስተምረውናልና /ኤፌ.፮፥፲፮/፣ የእምነት ጋሻችንን እናነሣለን፡፡ ደግሞም  ‹‹የጦር ዕቃችን ሥጋዊ አይደለምና፥ ምሽግን ለመስበር ግን በእግዚአብሔር ፊት ብርቱ ነው፤›› /፪ኛቆሮ.፲፥፬/ ተብሎ እንደ ተጻፈው መሣሪያችንም ሥጋዊ የጦር ትጥቅ ሳይኾን የዲያብሎስን የተንኮልና የክሕደት ምሽጎች ለመስበር የበረታው የእግዚአብሔር ቃል ነው፡፡ ስለዚህ ከእነዚህ ክንፍና ቅርፊት የሌላቸው ከተባሉት፤ ያለ መከላከያ ኾነው ራሳቸውን አስማርከው እኛንም ወደ እነርሱ ጥርጥርና ክሕደት ሊስቡ ወደሚሮጡት፤ ዳግመኛም የእግዚአብሔርን ቃል ምሥጢራት ወደማያመላልሱትና ሰኮና በተባለ ክሳደ ልቡናቸው መሬት ገቢርን ወደማይጨብጡት እንዳንጠጋ ‹‹እነርሱ ዅልጊዜም በነፍስ ርኩሳን ናቸው፤›› ተብሎ ተጽፎልናል፡፡ ‹‹ሠለስቱ ደቂቅን ከእሳት ያወጣቸው ማን ነው?›› ለሚለውን ጥያቄ ምላሽ የምንሰጠውም ‹‹ያመሰኳሉ›› የተባሉ ቅዱሳን የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ቃሉን እያመላለሱ መርምረው፣ ምሥጢሩን ከእግዚአብሔር ዘንድ ተረድተው እንደ ጻፉልን በማመንና በዚሁ (በእነርሱ) መንፈስ ይኾናል ማለት ነው፡፡

በእርግጥ ሠለስቱ ደቂቅን ከእሳት ያዳናቸው መልአክ ማን ነው?

መጀመሪያውንም መጽሐፍ ቅዱሱ ሠለስቱ ደቂቅን ከእሳት ያወጣቸው ‹‹ገብርኤል ነው›› አይልም፡፡ መጽሐፍ ቅዱሱ የሚለው የሚከተለውን ነው፤ ‹‹የዚያን ጊዜም ንጉሡ ናቡከደነፆር ተደነቀ ፈጥኖም ተነሣ፤ አማካሪዎቹንም፡- ‹ሦስት ሰዎች አስረን በእሳት ውስጥ ጥለን አልነበረምን?› ብሎ ተናገራቸው። እነርሱም፡- ‹ንጉሥ ሆይ እውነት ነው› ብለው ለንጉሡ መለሱለት። እርሱም፡- ‹እነሆ እኔ የተፈቱ በእሳቱም መካከል የሚመላለሱ አራት ሰዎች አያለሁ፤ ምንም አላቈሰላቸውም የአራተኛውም መልክ የአማልክትን ልጅ ይመስላል ብሎ መለሰ፤›› /ዳን.፫፥፳፬-፳፭/፡፡ በዚህ አገላለጽ መሠረት አራተኛውን ሰው ያየው ንጉሡ ናቡከደነፆር ሲኾን የጨመረበት ቃል ቢኖር ‹‹አራተኛው የአማልክትን ልጅ ይመስላል›› የሚለው ነው፡፡

ለመኾኑ አራተኛውን ሰው እርሱ ብቻ ለምን አየው? ሌሎቹ ለምን አላዩትም? የጥያቄው ቍልፍ ምሥጢር ያለው ከዚህ ላይ ነው፡፡ እውነቱን ለመናገር ይህ ሰው ጥንቱንም ሠለስቱ ደቂቅን ወደ እሳት የጣላቸው ሕዝቡን ለራሱ ምስል በማሰገድ ራሱን አምላክ አድርጎ ሊያስመልክ አስቦ ነበር፡፡ ታዲያ ራሱንና እርሱን የመሰሉትን አማክት አድርጎ የሚቈጥር ከኾነ የሚያየውን አራተኛውን  ሰው ‹‹የእኛን ልጅ ይመስላል›› ወይም ‹‹እኛን ይመስላል›› ለምን አላለም? ከዚያ ይልቅ አርቆ ሌሎች አማልክትን የሚያመልክ አስመስሎ ‹‹የአማልክትን ልጅ ይመስላል›› ያለበት ምሥጢር ምንድን ነው? ንጉሡ ይህን ያለበት ምክንያት እነርሱ ሳያዩት ከሠለስቱ ደቂቅ ጋር አራተኛ ሰው ወደ እሳቱ ገብቶ ሳይኾን ነገሩ የወልደ እግዚአብሔርን በሥጋ መገለጥ የሚያመላክት ምሥጢር ሳለለው ነው፡፡

በብሉይ ኪዳን ከተገለጹት ታላላቅ ሦስት የእግዚአብሔር መገለጦች ውስጥ ሦስተኛው ይህ የሠለስቱ ደቂቅ የድኅነት ታሪክ ነው፡፡ አንደኛው መገለጥ በመምሬ የአድባር ዛፍ ሥር እግዚአብሔር ለአብርሃም በሦስት ሰዎች አምሳል የተገለጠው መገለጥ ሲኾን /ዘፍ.፲፰/፣ ሁለተኛውም እግዚአብሔር ለአባታችን ለያዕቆብ በጐልማሳ አምሳል ተገልጾ ሲታገለው ያደረበት ታሪክና ያዕቆብም መጀመሪያ ‹‹ካልባረከኝ አልለቅህም›› ብሎ ከተባረከ በኋላ ‹‹‹እግዚአብሔርን ፊት ለፊት አየሁ፤ ሰውነቴም ድና ቀረች› ሲል የዚያን ቦታ ስም ‹ጵንኤል› ብሎ ጠራው፤›› ያሰኘው መገለጥ ነው /ዘፍ.፴፪፥፳፭-፴፪/፡፡ ሦስተኛው መገለጥ ደግሞ አላዊው የባቢሎን ንጉሥ ሠለስቱ ደቂቅን ወደ እቶነ እሳት በጣለበት ወቅት ያደረገው መገለጥ ነው፡፡

ሦስቱም መገለጦች የሚያመሳስሏቸው ሁለት ጠባይዓት አሏቸው፡፡ የመጀመሪያው በሦስቱም መንገድ እግዚአብሔር በሰው መልክና አምሳል መገለጡ ሲኾን ሁለተኛውና ዋነኛው ቃለ እግዚአብሔር በሥጋዌ (ሰው በመኾን) ተገልጦ ለሰው ፍጹም ድኅነት የሚሰጥ መኾኑን አስቀድሞ በምሳሌ መግለጥ ነው፡፡ መሠረታዊ መልእክቱ ደግሞ አምላክ ሰው ከኾነ በኋላ የሚያድነው የተስፋውን ዘር እስራኤልን ብቻ ሳይኾን አሕዛብንም ጭምር መኾኑን ለማሳየትና አሕዛብም የሥጋዌው ነገር ቀድሞ የተገለጠው ለእስራኤል ብቻ ስለ ኾነ እኛ ልናምንበት አይገባም እንዳይሉ ለዚህ ደንዳናና ጨካኝ ናቡከደነፆርም ጭምር ተገለጠለት፡፡

የነነዌ ሰዎች ታሪክም የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ኾኖ የተቀመጠውና እግዚአብሔር ለአሕዛብም ድኅነት ይፈጽም እንደ ነበር የተመዘገበው እግዚአብሔር የእስራኤል ብቻ ሳይኾን የዅሉም አምላክ መኾኑን ራሱ ብሉይ ኪዳንም ምስክር እንዲኾን ነው፡፡ እነዚህን የመሰሉ ሌሎች ታሪኮችና ምሳሌዎችም በብዛት በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ይገኛሉ፡፡ በዚህ በሠለስቱ ደቂቅ ድኅነት ውስጥ የታየው መገለጠጥ ዋነኛው ምሥጢርና መልእክትም የእግዚአብሔርን ሰው መኾንና አዳኝነት፤ እንደዚሁም እንደ ሠለስቱ ደቂቅ እሳትና ስለት፣ ሰይፍና ጐራዴ፤ እስራትና ግርፋት የሚቀበሉ ሰማዕታትን ዅሉ የሚያድናቸው እርሱ መኾኑን መግለጽ ነው፡፡ ታዲያ ዋነኛው መልእክቱና ምሥጢሩ ይህ ከኾነ ገብርኤልም ኾነ ሌሎቹ መላእክት ለምን ሠለስቱ ደቂቅን ከእሳት አወጡ (አዳኑ) ይባላሉ? በቅዱሳት መጻሕፍት ምስክርነት መሠረት ለሰዎች ከጊዜያዊና ምድራዊ አደጋና ሰዎች ከሚያመጡባቸው መከራ ድኅነት ሲደረግላቸው ድኅነታቸውን የሚፈጽሙላቸው ቅዱሳን መላእክት ማለትም ጠባቂ መላእክቶቻቸው ናቸው፡፡

ይህም ምንም እንኳን አንዳንድ ጊዜ በግልጽ፣ አንዳንድ ጊዜ ደግሞ በምሥጢር ቢገለጽም የእግዚአብሔር መላእክት ከሚጠብቋቸው ሰዎች ተለይተው አያውቁም፡፡ ለምሳሌ በሐዋርያት ሥራ ላይ ቅዱስ ያዕቆብን ያስገደለው ሄሮድስ ቅዱስ ጴጥሮስንም ለመግደል ባሰረው ጊዜ በዚያ ወቅት እንዲሞት እግዚአብሔር ስላልፈቀደ መልአኩ እንዲያድነው አድርጓል፡፡ ‹‹እነሆም የጌታ መልአክ ቀረበ፤ በቤትም ውስጥ ብርሃን በራ፡፡ ጴጥሮስንም ጎድኑን መትቶ አነቃውና ‹ፈጥነህ ተነሣ› አለው። ሰንሰለቶቹም ከእጁ ወደቁ። መልአኩም፡- ‹ታጠቅና ጫማህን አግባ› አለው፤ እንዲሁም አደረገ። ‹ልብስህንም ልበስና ተከተለኝ› አለው። ወጥቶም ተከተለው፡፡ ራእይንም የሚያይ ይመስለው ነበር እንጂ በመልአኩ የሚደረገው ነገር እውነት እንደ ኾነ አላወቀም። የመጀመሪያውንና የሁለተኛውንም ዘብ አልፈው ወደ ከተማ ወደሚያወጣው ወደ ብረቱ መዝጊያ ደረሱ፤ እርሱም አውቆ ተከፈተላቸው፡፡ ወጥተውም አንዲት ስላች አለፉ፡፡ ወዲያውም መልአኩ ከእርሱ ተለየ። ጴጥሮስም ወደ ልቡ ተመልሶ፦ ‹ጌታ መልአኩን ልኮ ከሄሮድስ እጅና የአይሁድ ሕዝብ ይጠብቁት ከነበረው ዅሉ እንደ አዳነኝ አሁን በእውነት አወቅሁ› አለ፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ /ሐዋ.፲፪፥፯፲፩/፡፡

ይቆየን

ሠለስቱ ደቂቅን ከእሳት ያዳናቸው መልአክ ማን ነው? – ክፍል አንድ

በዲያቆን ብርሃኑ አድማስ

ታኅሣሥ ፳፩ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በአንድ ወቅት በተሐድሶ መናፍቃን በተሰራጨ አንድ የቪዲዮ ቁራጭ ላይ በሦስቱ ድርሳናት ማለትም በድርሳነ ገብርኤል ላይ ገብርኤል፤ በድርሳነ ሚካኤል ላይ ሚካኤል፤ በድርሳነ ሩፋኤል ላይ ደግሞ ሩፋኤል ሠለስቱ ደቂቅን ከእሳት አዳናቸው ተብሎ ስለ ተገለጸ ‹‹ትክክለኛው ትምህርት የትኛው ነው? ሠለስቱ ደቂቅን ከእሳት ያዳናቸው መልአክስ ማን ነው?›› የሚል ጥያቄ በተደጋጋሚ ሲነሣ ሰምተናል፡፡

ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ደግሞ በዚህ ጽሑፍ በዋናነት የምንመለከተውን የመሰሉ ጥያቄዎችን እያነሡ ገድላትን፤ ድርሳናትንና ሌሎች አዋልድ መጻሕፍትንም የሚነቅፉና የሚያስነቅፉ ሰዎች ቍጥራቸው በርከት እያለ መጥቷል፡፡ ከዚህም የተነሣ በተለያዩ ሚዲያዎች የተለያዩ ጽሑፎችና የምስል ወድምፅ ስብከቶች ይቀርባሉ፡፡ ይህም ስለ ቅዱሳት መጻሕፍት ትርጓሜ ወይም ምሥጢራት ግንዛቤአችን አነስተኛ የኾነብንን ሰዎች ሊረብሸን ይችላል፡፡ እኛም ነገሩን ከመሠረቱ ለመረዳት እንዲያመቸን ቅዱሳት መጻሕፍት ላይ የሚነሡ ጥያቄዎችን ብቻ ሳይኾን የማንጠየቃቸውንም ጭምር በአግባቡ ተረድተን እንድንጠቀም የሚረዳ መንገድ ለመጠቆም ይህንን ጽሑፍ አዘጋጅተናል፡፡ አስቀድመንም ቅዱሳት መጻሕፍትን እንዴት ልንረዳ እንደምንችል ለማመላከት እንሞክራለን፤

በቅዱሳት መጻሕፍት ንባብ ሦስት ዓይነት መልእክቶችን እናገኛለን፡፡ የመጀመሪያው ታሪካዊ መልእክት ሲኾን ይህም ማለት ድርጊትን ሲዘግብልን ወይም የተጻፈው ደረቅ ትንቢትና ቀጥተኛ ትምህርት ማን መቼ ለማን በምን ምክንያት እንደ ተናገረው ስናጠና የምናገኘው ታሪካዊና ተጨባጭ መልእክት ነው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ ምግባራዊ መልእክት ሊባል የሚችለውና ምን ማድረግ እንዳለብን ወይም እንደሌለብን፤ እንዴትና መቼ ትእዛዛትን መፈጸም እንደሚገባን የሚያስተምረን ቀጥታ ልንተገብረው የሚገባንን ተግባር የሚያሳውቀን መልእክት ነው፡፡ ሦስተኛውና የመጨረሻው ደግሞ ምሥጢራዊ ወይም መንፈሳዊ መልእክት ነው፡፡ የዚህም ዋና ዓላማው ምሥጢሩን ከተረዳን በኋላ በገቢር (በተግባር) እንድንገልጸው ቢኾንም ዋናውን መልእክት የምናገኘውም ምሳሌው ወይም ትንቢቱ ወይም ታሪኩ በውስጡ አምቆ የያዘው መለኮታዊ መልእክትን ስናውቅ ነው፡፡ ይህ ምሥጢራዊ ወይም መንፈሳዊ መልእክት ግን በግምት ወይም በመላምት የሚሰጥ ሳይኾን ከጥንት ከጌታችንና ከሐዋርያት ጀምሮ እነዚህን መጻሕፍት ያስተማሩ ቅዱሳን አባቶች በመንፈስ ቅዱስ ተመርተው ከተናገሩትና ካስተማሩት ትምህርት የሚገኝ ነው፡፡

ለምሳሌ ጌታችን ሉቃስንና ቀልዮጳን ወደ ኤማሁስ ከሚሔዱበት መንገድ የመለሳቸው እነርሱ እንደ ተናገሩት ‹‹ቅዱሳት መጻሕፍትን እየተረጐመ›› ሲነግራቸውና በምሥጢራቱም ‹‹ልቡናቸውን ካቃጠለው›› በኋላ ነው /ሉቃ.፳፬፥፲፫-፴፭/፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያትም መልእክቶቻቸውንና ወንጌሎቻቸውን ብናይ በኦሪት የምናውቃቸውን ታሪኮችና ትእዛዛት መንፈሳዊና ምሥጢራዊ መልእክቶቻቸውን በሰፊው አስቀምጠውልናል፡፡ ለምሳሌ ቅዱስ ጳውሎስ እስራኤል ከግብጽ ሲወጡና ባሕረ ኤርትራን ሲሻገሩ የገጠማቸውን ነገር በሙሉ የጥምቀትና የመንፈሳዊ ወይም የጸጋ እግዚአብሔር ምግብና እንደ ኾነ ተርጕሞልናል /፩ኛቆሮ.፲፥፩-፭/፡፡ አጋርንና ሣራንም የኦሪትና የወንጌል ምሳሌዎች አድርጎ ልጆቻቸው እስማኤልና ይስሐቅ ለምን ዓይነት መንፈሳዊና ታላቅ ምሥጢራዊ መልእክት ምሳሌዎች እንደ ኾኑ ነግሮናል /ገላ.፬፥፳፪ እስከ ፍጻሜው/፡፡

የኋላ ሊቃውንትም በዚሁ በእነርሱ መንገድ ሔደው የቅዱሳት መጻሕፍትን ተዝቆ የማያልቅ መለኮታዊ መልእክት ወይም ምሥጢር በስፋት አስተምረውናል፡፡ አባታችን ያዕቆብ በፍኖተ ሎዛ ሌሊት በሕልሙ ከላይ እግዚአብሔር ተቀምጦባት መላእክት ሲወጡባት ሲወርዱባት ያያትን መሰላል በሦስተኛው ክፍለ ዘመን መጨረሻ ላይ የሚላኖ ሊቀ ጳጳስ የነበረው ቅዱስ አምብሮዝ ሲተረጕም፡- ‹‹መላእክት የተባሉት ከሐዋርያት ጀምሮ ያሉ ቅዱሳን ሊቃውንት ናቸው፡፡ የመሰላሉ ቋሚዎች የብሉይና የሐዲስ መጻሕፍት ሲኾኑ በቋሚዎቹ ላይ ያሉ ርብራቦች ደግሞ ከእነርሱ የሚገኙት ምግባራት ማለትም ጾም፣ ጸሎት፣ ቀዊም፣ ስግደትና የመሰሉት ናቸው፡፡ ሊቃውንት በእነዚህ በኩል ወደ ላይ በብቃት ይወጣሉ፤ እንደ ቅዱስ ጳውሎስም እስከ ሦስተኛው ሰማይ ይነጠቃሉ፡፡ ምሥጢራተ መጻሕፍትንም ይዘውልን ይወርዳሉ፤›› በማለት ያስረዳል፡፡

ቅዱሳት መጻሕፍት ምሥጢራዊ መልእክት አላቸው ሲባልም አንድ ሰው ከራሱ ዓለማዊ ዕውቀት ወይም ልምድ ብቻ ተነሥቶ ወይም ከአስተሳሰቡ አመንጭቶ የሚነግረን ሳይኾን ቅዱሳን ሊቃውንት ከእግዚአብሔር በተሰጣቸው ጸጋ መሠረት ከእርሱ ተቀብለው የሚሰጡን ትምህርት ነው፡፡ ምክንያቱም ቅዱሳት መጻሕፍት በሰው ቋንቋ የተጻፉ የእግዚአብሔር መለኮታዊ መልእክቶች ናቸውና ከቃላቱ መደበኛ ትርጕም ያለፈውን መለኮታዊ ምሥጢር ወይም መልእክት ልናገኘው የምንችለው ከእግዚአብሔር በሚሰጥ ጸጋ ብቻ ስለሚኾን ነው፡፡ በመጠኑም ቢኾን ስለ ትርጓሜ መጻሕፍት ምሥጢር ይህን ያህል ከጠቀስን አሁን ደግሞ ከላይ በርእሱ ስለ ተቀመጠው የኦሪት ጥቅስ ምሥጢራዊ መልእክት እንመልከት፤

በቅዱሳት መጻሕፍት ስለምንቀበለውና ስለማንቀበለው ትምህርት ከተነገረባቸው መንገዶች አንደኛው ምሳሌያዊ መንገድ ነው፡፡ ይህም ማለት ለጊዜው ቀጥታ ለሚተገበር ምግባራዊ ሕግ የተሰጡ መስለው ምሳሌነታቸውና ምሥጢራዊ መልእክታቸው ግን ሃይማኖታዊ ወይም ስለ ሃይማኖታችን ልንቀበላቸውና ላንቀበላቸው ስለሚገባን ትምህርቶች በምሳሌ የተገለጹ መኾናቸው ነው፡፡ ከእነዚህ መልእክቶች አንደኛውን ለማስታወስ ያህል፡- ‹‹የተሰነጠቀ ሰኮና ያለውንና የሚያመሰኳውን እንስሳ ዅሉ ብሉ፤ ነገር ግን ከሚያመሰኩት፣ ሰኮናቸው ስንጥቅ ከኾነው ከእነዚህ አትበሉም፡፡ ግመል ያመሰኳል፤ ነገር ግን ሰኮናው ስላልተሰነጠቀ በእናንተ ዘንድ ርኩስ ነው። ሽኮኮ ያመሰኳል፤ ነገር ግን ሰኮናው ስላልተሰነጠቀ በእናንተ ዘንድ ርኩስ ነው። ጥንቸልም ያመሰኳል፤ ነገር ግን ሰኮናው ስላልተሰነጠቀ በእናንተ ዘንድ ርኩስ ነው። እርያም ሰኮናው ተሰንጥቋል፤ ነገር ግን ስለማያመሰኳ በእናንተ ዘንድ ርኩስ ነው። የእነዚህን ሥጋ አትበሉም፤ በድናቸውንም አትነኩም፡፡ በእናንተ ዘንድ ርኩሶች ናቸው፤›› ተብሎ በኦሪት የተገለጸው ትእዛዝ ይገኝበታል /ዘሌ.፲፩፥፫-፰/፡፡

በኦሪት ሕግ እንድንመገባቸውና እንዳንመገባቸው ለማድረግ እግዚአብሔር ያዘዘን እያንዳንዳቸውን በሙሉ በመዘርዘር ሳይኾን በቡድን በመመደብና ምሳሌ በመጥቀስ ነው፡፡ እንድንበላቸው የተፈቀዱት እንስሳት ሁለት ነገሮችን ሊያሟሉ ይገባቸዋል፤ ይኸውም በኦሪት ዘሌዋውያን እንደ ተጻፈው የሚያመሰኩና ሰኮናቸው የተሰነጠቀ መኾን ይኖርባዋቸል፡፡ ሁለቱንም መሥፈርት የማያሟሉ ብቻ ሳይኾን ከሁለቱ አንዱንም የማያሟሉ እንስሳት አይበሉም፡፡ ይህ ትእዛዝም ቀደም ብለን ባየነው ትምህርት መሠረት ሦስቱን መልእክታት ያስተላልፋል፤ ታሪካዊ መልእክቱ ይህ ነገር ሕግ ኾኖ መቼ? በማን? ለማን እንደ ተሰጠና የመሳሰሉትን ምሥጢራት ሲነግረን፣ ምግባራዊ መልእክቱ ደግሞ የፈጠራቸውን የሚያውቅ አምላክ ሳስቶና ወይም ተመቅኝቶን ሳይኾን እንስሳቱ በሰውነታችን ላይ በሚያመጡት ጉዳትና በመሳሳለው ችግር ምክንያት እንዳይበሉ አዝዞናል፡፡

ዳግመኛም በዘመነ ኦሪት እነዚህን እንስሳት መብላትና አለመብላት የመርከስና የመቀደስ ዋና ምክንያትም ነበረ፡፡ በሐዲስ ግን የማይበሉትን እንኳ የማንበላው ጥንቱንም ስለማይጠቅሙን ነው (ምንም ሲበሉ የኖሩትን ክርስቲያን ማድረጉ ወይም ክርስትና የሚቀድሳቸው መኾኑ የታወቀ ቢኾንም የማይበሉ የነበሩት ይብሉ ማለት አይደለምና) አይጠቅሙንምና አሁንም አንበላቸውም፡፡ ሐዋርያትም በዲድስቅልያ፡- ‹‹ወቦ እለ ይብሉ ሥጋ አኅርው ንጹሕ ባሕቱ ኢኮነ ንጹሐ አላ ርኩስ መፍትው ለነ ንርኀቅ እምዘ ከመዝ ግብር ወዘሰ ኮነ ንጹሐ በውስተ ሕግ ይብልዑ እምኔሁ፤ የእሪያዎች ሥጋ ንጹሕ ነው የሚሉ አሉ፤ ነገር ግን ርኩስ ነው እንጂ ንጹሕ አይደለም፡፡ ከእንደዚህ ያለ ሥራ እንርቅ ዘንድ ይገባናል፡፡ በመጽሐፍ ንጹሕ ከኾነ ግን ከእርሱ ይብሉ፤›› ሲሉ አዝዘውናል / አንቀጽ ፴፪፥፵፮-፵፯/፡፡

በዚህ ኃይለ ቃል ‹‹የሚያመሰኩና ሰኮናቸው የተሰነጠቀ ንጹሐን ናቸው›› የተባሉት በሃይማኖትና በምግባር የሚኖሩ መምህራንና ምእመናን ናቸው፡፡ የሚያመሰኳ (በአሁኑ አማርኛ የሚያመነዥክ ሲባል የምንሰማው ነው) ማለትም የቅዱሳት መጻሕፍትን ምሥጢራት በሕሊናው የሚያመላልስ ማለት ነው፡፡ የሚያመነዥክ ወይም የሚያመሰኳ እንስሳ ሣሩንም ቅጠሉንም ከበላው በኋላ እንደ ገና ወደ ላይ ወደ አፉ እያመጣ ደጋግሞ እንደሚያላምጠው ቅዱሳንና እውነተኛ መምህራንም አንዴ በትምህርት የተቀበሉትን ምሥጢር ወይም ቃለ መጽሐፍ በሚገባ ከተረዱትና በልቡናቸው ካሳደሩት በኋላ ምሥጢሩን ወደ ሕሊናቸው እያመላለሱ፣ እያወጡና እያወረዱ የበለጠ እያራቀቁ ለራሳቸውም ለሌላውም ጤናና ሕይወትን የሚሰጥ ተስማሚ ምግብ ያደርጉታል፡፡ ‹‹ብፁዕ ብእሲ … ወዘሕጎ ያነብብ መዓልተ ወሌሊተ፤ ሕጉን ወይም ቃሉን በሌሊትም በቀንም የሚያስብ (ምሥጢራቱን የሚረዳ) ምስጉን፣ ንዑድ፣ ክቡር ነው፤›› እንዳለ ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ /መዝ.፩፥፫/፡፡

ሰኮናው የተሰነጠቀ ማለት ደግሞ በተራመደ ጊዜ መሬት በደንብ የሚቆነጥጥ፣ የሚጨብጥ ማለት ነው፡፡ ይህም ማለት የሚናገረውንና የሚያውቀውን በሕይወቱ ተግባራዊ አድርጎ የሚኖርበት ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ዳዊት ከላይ ከተጠቀሰው መዝሙሩ በማከታተል፡- ‹‹ወይከውን ከመ ዕፅ እንተ ትክልት ኀበ ሙሐዘ ማይ፤ እንት ትሁብ ፍሬሃ በበጊዜሃ ወቈጽላኒ ኢይትነገፍ፤ እርሱም በውኃ ፈሳሾች ዳር እንደ ተተከለች፣ ፍሬዋን በየጊዜዋ እንደምትሰጥ፣ ቅጠልዋም እንደማይረግፍ ዛፍ ይኾናል፤ የሚሠራውም ዅሉ ይከናወንለታል፤›› እንደ ጠቀሰው ማለት ነው /መዝ.፩፥፫/፡፡

የማያመሰኳ እንስሳ የዋጠውን መልሶ እንደማያደቀው መልሶ መላልሶ እንደማያኝከው ዅሉ መናፍቃንም አንድ ጥቅስን በኾነ መንገድ ጐርሰው ከዋጡት በኋላ ምሥጢር አያመላልሱም፤ ደጋግመውም አያኝኩትም፡፡ ማለትም የሚመላለሱ ምሥጢራትን አያገኙም፤ አይመረምሩም፡፡ ዳግመኛም ሰኮናቸው ስላልተሰነጠቀ መሬት አይቆነጥጡም፤ ሃይማኖቱንም በምግባር አይኖሩትም፤ እንዲሁ ሲያደናግሩ ይኖራሉ እንጂ፡፡ ይህም ማለት እንደ ግመል በአካል ገዝፈው ብናያቸውም ለሰኮናቸው የሚስማማ አሽዋ (ያልረጋ ልቡና) ፈልገው በዚያ ይኖራሉ እንጂ እንደ ሌሎቹ እንስሳት መሬት ቆንጥጠው ረግጠው ገደልና ተራራ አይሻገሩም፤ ሃይማኖት አቀበትን ሊወጡ ገደላ ገድል ተጋድሎዎችንም አልፈው ለምሥጢር፣ ለክብር ሊበቁ አይችሉም፡፡ በሃይማኖት ገና ያልረጋና እንደ አሸዋ የሚንሸራተት ልቡና ካለ የመናፍቃን ድፍን ሰኮና ይረግጠዋል፤ የበለጠም ያንሸራትተዋልና ዅላችንም ልቡናችንን ለማጽናት መትጋት ይገባናል፡፡

ከዚሁ ከሚበሉና ከማይበሉ እንስሳት ምሥጢር ሳንወጣ በባሕር ውስጥ ካሉት እንስሳት መካከል እንድንበላቸው የተፈቀዱልን ቅርፊትና ክንፍ ያላቸው ዓሦች ናቸው፡፡ ቅርፊት ለባሕር ፍጥረታት ጋሻቸው መጠበቂያቸው እንደ ኾነ ዅሉ በክርስትናም ከመናፍቃን የኑፋቄ ጦርና የክሕደት መርዝ ለመዳን የሃይማኖትና የምግባር ጋሻ መታጠቅ ያስፈልጋል፡፡ ዓሦች በክንፋችው ከላይኛው የባሕር ክፍል ድረስ እንደሚንሳፈፉበትና ወደ ታች እንዳይዘቅጡ እንደሚጠበቁበት ዅሉ በመንፈሳዊ ሕይወትና በንጽሕና ክንፍ ወደ ከፍተኛው የእግዚአብሔር ምሥጢርና መረዳት የማይወጡ እንደ ድንጋይ በከበደ በዚህ ዓለም ፍልስፍና እና ሥጋዊ ሙግት ወደ መሬታዊነትና ሥጋዊነት የሚዘቅጡት መናፍቃን ‹‹ርኩሳን›› ከሚባሉት መመደባቸውን ማወቅ፣ አውቆም ከኑፋቄ ትምህርታቸው መጠበቅ ተገቢ ነው፡፡ ከላይ እንደ ገለጽነው እነርሱ ከዘመን አመጣሽ ሐሳብና ክሕደት የሚጠበቁበት ቅርፊት (የሃይማኖት ጋሻ) የሌላቸው ናቸውና፡፡

አንዳንዶቹ ‹‹አስኳሉን እንስጣችሁ ስንላቸው ቅርፊቱን አትንኩብን አሉ›› ሲሉ እንደሚደመጡት፣ (በኤግዚቢሽን ማእከል በተደረገው የተሐድሶዎች ልፈፋ ላይ አንድ አባ ተብየ የተናገረውን አስታውሱ) ቅርፊቱ የእንቁላሉን አስኳል የያዘውና ከጉዳት የሚጠብቀው አካል መኾኑን እንኳ ማሰብ ተስኗቸው መጠበቂያ ቅርፊት የሌላቸው ብቻ ሳይኾኑ ካላቸውም ላይ መስበር የሚፈልጉ መኾናቸውን መንፈስ ቅዱስ ፊታቸውን ጸፍቶ፣ አፋቸውን ከፍቶ አናግሯቸዋል፤ በራሳቸውም ላይ አስመስክሯቸዋል፡፡

ስለዚህ ክርስቲያኖች ንጹሐን የሚበሉ (አምላካቸው የሚቀበላቸው) የሚኾኑት ጥርጥርንና ክሕደትን፣ ይህንም የመሰለ የመናፍቃንን የመዘባበትና የክሕደት ጦር የሚከላከል በቅርፊት የተመሰለ የሃይማኖት ጋሻ ሲኖረን ነው፡፡ ከጋሻዎቻችን ዋነኛው መሣሪያ ደግሞ የሃይማኖታችንን ነገር፣ የቅዱሳት መጻሕፍትንም ምሥጢር ለብሶ ማለትም አውቆ መገኘት ነውና ጊዜ ወስዶ ቁጭ ብሎ መማር እንኳ ባይቻል በተገኘው አጋጣሚ ዅሉ ልቡናን ከፍቶ በወሬና በአሉባልታ ሳይጠመዱ መማር፣ መጠየቅና እንደ ተገለጸው እያመላለሱ በማኘክ (በማጥናት) ቃሉን በሚገባ መያዝ ተገቢ ነው፡፡ ከዚህም በላይ በሃይማኖት ልብን ማጽናት ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባ ጉዳይ ነው፡፡ ይህ ከኾነ ጠይቀን ያልገባንንና የማናውቀውን ምሥጢር እስከምንረዳው ድረስ ጊዜ እናገኛለን፡፡

ነገር ግን ብዙዎቻችን ትዕግሥት የለንም፤ ዛሬ ይህን ጽሑፍ ከምናነብበው እንኳ አንዳንዶቻችን ቀጥታ ነገሩን በቅርቡ ማግኘት ባለመቻላችን ልንበሳጭም እንችላለን፡፡ ነገር ግን አሁንም አስቀድመን አንዲት ጥያቄ ብቻ መልሰን እንሒድ፤

ይቆየን

የአዳዲስ አማንያኑ ቍጥር ወደ ሰማንያ አምስት ሺሕ አደገ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ታኅሣሥ ፳ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

img_0090

በማኅበረ ቅዱሳን አስተባባሪነት በተከናወነው የጥምቀት መርሐ ግብር ከመስከረም እስከ ታኅሣሥ ወር ፳፻፱ ዓ.ም ባለው የአገልግሎት ዘመን በመተከል ሀገረ ስብከት በአምስት ወረዳዎች ውስጥ በሚገኙ ዐሥር የጥምቀት ቦታዎች ስድስት ሺሕ ስምንት መቶ ሃያ አንድ፤ በጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከት በዐርባ ምንጭ አካባቢ ሁለት ሺሕ አንድ መቶ ሠላሳ ሰባት፤ በደቡብ ኦሞ ሀገረ ስብከት በጂንካ አካባቢ አንድ ሺሕ ስልሳ አንድ፤ በሸካ ቤንች ማጂ ሀገረ ስብከት በማጂ ወረዳ ሦስት ሺሕ ስድስት መቶ ሰማንያ ስድስት፤ በድምሩ ዐሥራ ሦስት ሺሕ ሰባት መቶ አምስት በልዩ ልዩ ጠረፋማ አካባቢዎች የሚኖሩ አዳዲስ አማንያን የሥላሴ ልጅነትን አግኝተዋል፡፡

ይህም ከአሁን በፊት ማኅበሩ ካስጠመቃቸው ሰባ ሁለት ሺሕ አማንያን ጋር ሲደመር የአዳዲስ አማንያኑን ቍጥር ወደ ሰማንያ አምስት ሺሕ ሰባት መቶ አምስት እንደሚያደርሰው በማኅበሩ የስብከተ ወንጌል ትግበራ ባለሙያ ቀሲስ ይግዛው መኮንን ለዝግጅት ክፍላችን አስታውቀዋል፡፡ ከዐሥራ ሦስት ሺሕ ሰባት መቶ አምስቱ አዳዲስ አማንያን መካከልም ከፊሎቹ ታኅሣሥ ፱፣ ፲፮ እና ፲፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም የተጠመቁ ናቸው፡፡

metekel-2

የመተከል ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ መልአከ ሰላም ብርሃን ዓለም ጥምቀቱ በተፈጸመበት ዕለት በድባጤ ወረዳ ቤተ ክህነት አልባሳ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ተገኝተው ትምህርተ ወንጌል ሲሰጡ ‹‹ዛሬ ወላጆች ከልጆቻችሁ ጋር ተጠምቃችኋል፡፡ ከዚህ በኋላ ልጆችን ስትወልዱ ወንዶችን በዐርባ፤ ሴቶችን ደግሞ በሰማንያ ቀናቸው ወደ ቤተ ክርስቲያን በማምጣት ማስጠመቅ አለባችሁ፤›› በማለት ተጠማቂዎቹን አስተምረዋል፡፡ በማያያዝም ተጠማቂዎቹ በክርስቲያናዊ ምግባር ጸንተው፣ ከኀጢአት ተለይተው መኖር እንደሚገባቸው፤ ከዚህም ባሻገር ያልተጠመቁ ዘመዶቻቸውንና ጎረቤቶቻቸውን አስተምረው ወደ ክርስትና ሃይማኖት መመለስ፤ የተጠመቁትንም በሃይማኖትና በምግባር እንዲጸኑ ማድረግ እንደሚጠበቅባቸው ሥራ አስኪያጁ ተጠማቂዎቹን መክረዋል፡፡

በመተከል ሀገረ ስብከት በተካሔደው የጥምቀት መርሐ ግብር ከልዑካኑ ጋር አብረው የተሳተፉት የማኅበረ ቅዱሳን ምክትል ዋና ጸሐፊ አቶ ንጉሤ መብራቱ አዳዲስ አማንያንን ማስጠመቅ ማኅበረ ቅዱሳን ከሚሰጠው አገልግሎት ውስጥ ዐቢዩና ዋነኛው ተግባር መኾኑን አስታውሰው ለአገልግሎቱ ውጤታማነትና ለተጠማቂዎቹ ቍጥር መጨመርም የማኅበሩ አባላትና የበጎ አድራጊ ምእመናን ተሳትፎ ከፍተኛ አስተዋጽዖ እንዳለው ተናግረዋል፡፡

metekel-3

የማኅበረ ቅዱሳን የግልገል በለስ ማእከል ሰብሳቢ አቶ አሰፋ ደሳለኝ እና ጸሐፊው አቶ ደግ አረገ አለነ በበኩላቸው ማእከሉ ከመተከል ሀገረ ስብከት ጋር ኾኖ ሰባክያንን በመመደብ፣ ቅኝት በማድረግና በመሳሰሉት ተግባራት አገልግሎቱን በማስተባበር የሚጠበቅበትን ድርሻ መወጣቱን ጠቅሰው ማእከሉ ያለበት የሰው ኃይል፣ የመምህራንና የገንዘብ እጥረት፣ እንደዚሁም የጥምቀት መርሐ ግብሩ የሚፈጽምባቸው ቦታዎች ርቀትና ለአገልግሎት ምቹ አለመኾን አዳዲስ አማንያንን የማስጠመቁን ተልእኮ ከሚፈታተኑ ችግሮች መካከል ዋነኞቹ መኾናቸውን ጠቁመዋል፡፡

በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል የስብከተ ወንጌል አገልግሎት በመስጠት ላይ ከሚገኙ ሰባክያነ ወንጌል መካከል ዲያቆን ቶማስ ጐሹ እና ወንድም ፈጠነ ገብሬ ተጠማቅያኑ ቀደምት አባቶቻቸው ለዚህ ክብር ሳይበቁ በማለፋቸው እንደሚቈጩና የክርስትና ጥምቀትን ለማግኘት ሲሉም ከሌሊቱ ሰባት ሰዓት ጀምረው በእግራቸው እንደ ተጓዙ ገልጸው የጉሙዝ ብሔረሰብ አባላት የቃለ እግዚአብሔር ጥማት እንዳለባቸውና ‹‹ልጆቻችንን የቄስ ትምህርት አስተምሩልን?›› እያሉ እንደሚጠይቋቸውም አስረድተዋል፡፡

ወደ ፊትም ሰንበት ት/ቤቶችን በየቦታው በማቋቋም ተጠማቅያኑ በሃይማኖታቸው እንዲጸኑ ለማድረግ ዕቅድ ቢኖራቸውም ነገር ግን ሰባክያነ ወንጌል በብዛት አለመመደባቸው፣ ቢመደቡም የሚከፈላቸው የድጎማ ገንዘብ አነስተኛ መኾኑ፣ ሞተሮቻቸው ሲበላሹባቸው የሚያስጠግኑበት በጀት አለመኖሩ፣ እንደዚሁም የአካባቢው መናፍቃን ተጽዕኖ መበራከቱ ‹‹አገልግሎታችንን በአግባቡ እንዳንወጣ አድርጎናልና መፍትሔ እንፈልጋለን›› ሲሉ የድጋፍ ጥያቄ ያቀርባሉ፡፡

metekel-2

ከተጠማቅያን የጉሙዝ ብሔረሰብ አባላት መካከል አንደኛው ለዚህ ታላቅ ክብር ስላበቃቸው እግዚአብሔርን ካመሰገኑ በኋላ ‹‹አጥምቃችሁን መመለስ ብቻ ሳይኾን ለወደ ፊትም አስተማሪ፣ መካሪ ካህን አጥተን ወደ ሌላ ቤተ እምነት እንዳንወሰድ እየመጣችሁ በመምከር፣ በማስተማርና በማበረታታት በሃይማኖታችን እንድንጸና ድጋፍ አድርጉልን፤›› ሲሉ የድረሱል ድምፃቸውን ያሰማሉ፡፡ ሌላኛው ተጠማቂ ወንድምም እንደዚሁ ራሳቸውን ጨምሮ ዐሥራ አራት የቤተሰቡ አባላት በሙሉ በአንድ ቀን መጠመቃቸውን አውስተው ‹‹ያልተጠመቁ ዘመዶቼና ወዳጆቼንም ተምረው የሥላሴን ልጅነት እንዲያገኙ አደርጋለሁ›› ብለዋል፡፡

የማኅበሩ ጋዜጠኞችም በመተከል ሀገረ ስብከት ልዩ ልዩ ቦታዎች ታኅሣሥ ፲፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በተካሔደው የጥምቀት መርሐ ግብር በተሳተፍንበት ወቅት በድባጤ ወረዳ ቤተ ክህነት በአልባሳ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን የአዊ ብሔረሰብ ተወላጆች ተጠማቂ የጉሙዝ ብሔረሰብ ተወላጆችን ክርስትና በማንሣት በሚያስፈልጋቸው መንፈሳዊና ማኅበራዊ ጉዳይ ዅሉ ከጎናቸው እንደማይለዩ ቃል በመግባት ዝምድናቸውን ሲያጠናክሩና አንድነታቸውን ሲያጸኑ ተመልክተናል፡፡

img_0143በግል መኪኖቻቸው ልዑካኑን በመያዝ በጉዞው የተሳተፉ ወንድሞችም ከአሁን በፊት ብዙ ቦታዎችን እንደሚያውቁ፤ ነገር ግን እንደዚህ ዓይነት አስቸጋሪ መንገድ እንዳላጋጠማቸውና መንገዱም ከጠበቁት በላይ ለመኪናዎቻቸው አስቸጋሪ እንደ ነበረ ገልጸው ማኅበሩ የሚሰጠውን አገልግሎት በመመልከት በመንፈሳዊ ቅናት ተነሳሥተው ብዙ ውጣ ውረዶችን በመቋቋም ተልእኳቸውን ተወጥተው መመለሳቸውን ተናግረዋል፡፡ ባለ መኪኖቹ ‹‹መንፈሳዊ ጉዞው ወደ ፊት የሚጠበቅብንን ክርስቲያናዊ ሓላፊነት ለመወጣት እንድንዘጋጅ አድርጎናል›› ሲሉም ቃል ገብተዋል፡፡

የጥምቀት መርሐ ግብሩን ለማስተባበር በየጠራፋማ አካባቢዎች ተሰማርተው ለነበሩ የማኅበረ ቅዱሳን ልዑካንም የማኅበሩ ሥራ አመራርና ሥራ አስፈጻሚ አባላት፣ የልዩ ልዩ ዋና ክፍሎች አገልጋዮችና ተጋባዥ እንግዶች በተገኙበት በማኅበሩ ሕንጻ ፮ኛ ፎቅ አዳራሽ የእንኳን ደኅና መጣችሁ አቀባበል ተደርጎላቸዋል፡፡

በዕለቱ የማኅበሩ ዋና ጸሐፊ አቶ ተስፋዬ ቢኾነኝ የማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎት በምቹ ኹኔታዎች የሚፈጸም ተግባር ሳይኾን ፈተና የበዛበት ተልእኮ መኾኑን ገልጸው ልዩ ልዩ ፈተናዎችም ማኅበሩ መንፈሳዊ ተልእኮውን በአግባቡ እንዲወጣ ስላደረጉት በሺሕ የሚቈጠሩ ኢአማንያን የሥላሴ ልጅነትን እንዲያገኙ ለማድረግ መቻሉን አስረድተዋል፡፡

metekel

‹‹በጠረፋማ የኢትዮጵያ አካባቢዎች በልዩ ልዩ ቋንቋ ወንጌልን የሚሰብኩ መምህራን የሕይወት መጻሕፍት ናቸውና ዅላችንም ልንማርባቸው ይገባል፤›› ያሉት ዋና ጸሐፊው በጸሎት፣ በስብከት፣ በማስተባበር፣ በገንዘብ ድጋፍ፣ በጉልበት ሥራና በመሳሰሉት ተግባራት በመሳተፍ ለአማንያኑ መጠመቅ ከፍተኛ አስተዋጽዖ ያበረከቱ የቤተ ክርስቲያን አባቶችን፣ መምህራንና ካህናትን፣ እንደዚሁም በጎ አድራጊ ምእመናንን በማኅበሩ ስም አመስግነዋል፡፡

ከሥራ አመራር አባላት መካከል አንደኛው ከፈጸምነው ተልእኮ ይልቅ ገና ያልሠራነው ብዙ ተግባር እንደሚበልጥ በመገንዘብና ምእመናንን ከቤታቸው ለማስወጣት ተግተው የሚሠሩ አካላት በየቦታው እንደሚገኙ በመረዳት ወደ ፊት ለሚጠበቅብን ዘርፈ ብዙ ሥራ መዘጋጀት ተገቢ መኾኑን አስረድተዋል፡፡

አያይዘውም በጥምቀት መርሐ ግብሩ የተሳተፉ መምህራን፣ ጋዜጠኞች፣ የካሜራ ባለሙያዎች፣ ሹፌሮችና ሌሎችም የልዑካኑ አባላት በአገልግሎቱ መሳተፋቸው ምስጋና ለማግኘት ሳይኾን እናት ቤተ ክርስቲያናቸውን በተሰማሩበት የሥራ ዘርፍ ለማገልገል እና ክርስቲያናዊ ግዴታቸውን ለመወጣት መኾኑን ሊረዱት እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡

metekel

ተጠማቂዎቹ እንዳይበተኑና በሃይማኖታቸው እንዲጸኑ ለማድረግ በጠረፋማ አካባቢዎች አብያተ ክርስቲያናትን ማሳነጽ፣ በየቋንቋው የሚሰብኩ መምህራንና ካህናትን ቍጥር ማሳደግ፣ የትምህርተ ሃይማኖት መማሪያ መጻሕፍትን በየቋንቋው ማዘጋጀት፣ አዳሪ ት/ቤቶችንና ሰንበት ት/ቤቶችን በየቦታው ማቋቋም፣ የስብከት ኬላዎችን ማስፋፋትና ለተጠማቅያኑ አስፈላጊውን ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ድጋፍ ማድረግ ለወደፊቱ በማኅበሩ ሊሠሩ የታቀዱ ተግባራት መኾናቸውን የትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ምክትል ሓላፊ አቶ ሰይፈ አበበ ጠቅሰው ይህንን ዕቅድ ከግብ ለማድረስም የበጎ አድራጊ ምእመናን ተሳትፎ እንዳይለያቸው በማኅበሩ ስም መንፈሳዊ ጥሪያቸውን አቅርበዋል፡፡

ሰማንያ አምስት ሺሕ ኢአማንያንን የቤተ ክርስቲያን ልጆች እንዲኾኑ ማድረግ ታላቅ ተልእኮ ቢኾንም ከዚህ የበለጠ መትጋት ከኹላችንም የሚጠበቅ ተግባር ነው፡፡ መላው ሕዝበ ክርስቲያን በአንድነት ኾነን ተባብረን ከሠራን ከዚህ በላይ ቍጥር ያላቸው ኢአማንያንን ለማስጠመቅና ተዋሕዶ ሃይማኖታችንን ይበልጥ ለማስፋፋት እንደሚቻል ማኅበረ ቅዱሳን ያምናል፡፡ ስለዚህም በትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ ፕሮግራም (መርሐ ግብር) ለሚሠሩ ልዩ ልዩ ፕሮጀክቶች መሳካት የበጎ አድራጊ ምእመናን ድጋፍ እንዳይለየን ሲል ማኅበሩ በቤተ ክርስቲያን ስም ጥሪውን ያስተላልፋል፡፡

ነገረ ድኅነት በትንቢተ ነቢያት (ካለፈው የቀጠለ)

ታኅሣሥ ቀን ፳፻፱ .

በመ/ ምሥጢረ ሥላሴ ማናየ

፬. ብርሃን

ነቢያት ዓለምን ለማዳን የመጣውን ሰማያዊ ንጉሥ ‹‹ብርሃን›› በማለት ጠርተውታል፡፡ ጨለማ የተባለ ዲያብሎስን ድል ነሥቶ ከሲኦል ባርነት ነጻ የሚያወጣቸው፤ ከኃጢአት ወደ ጽድቅ የሚመልሳቸው እርሱ ነውና፡፡ ቅዱስ ዳዊት ‹‹ለይኩን ብርሃኑ ለእግዚአብሔር አምላክነ ላዕሌነ፤ የአምላካችን የእግዚአብሔር ብርሃኑ በእኛ ላይ ይኹን›› (መዝ.፹፱፥፲፯) በማለት መዘመሩም ‹‹እግዚአብሔር ወልድ የሰውን ሥጋ ተዋሕዶ ያድነን›› ሲል ነው፡፡

አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ በፀሐይ ይመሰላሉ፡፡ ፀሐይ ክበብ፣ ብርሃንና ሙቀት አላት፤ ክቡ የአብ፣ ብርሃኑ የወልድ፣ ሙቀቱ ደግሞ የመንፈስ ቅዱስ ምሳሌ ነው፡፡ ብርሃን ከፀሐይ ሳይለይ ወደዚህ ዓለም መጥቶ ጨለማውን አሸንፎ በዚህ ዓለም ላሉት ዅሉ እንዲያበራ፤ በብርሃኑ ታግዘውም ሰዎች ዅሉ እንዲመላለሱበት እግዚአብሔር ወልድም ከሰማየ ሰማያት ወርዶ ከድንግል ማርያም ሲወለድ ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ህልውና አልተለየምና በብርሃን ተመስሏል፡፡

ቅዱስ ዳዊትም የኢየሱስ ክርስቶስን ብርሃንነት በሚመለከት ምሥጢር ‹‹ፈኑ ብርሃነከ ወጽድቀከ እማንቱ ይምርሐኒ ወይሰዳኒ ደብረ መቅደስከ ወውስተ አብያቲከ እግዚኦ፤ ብርሃንህን እና ጽድቅህን ላክ፤ እነርሱ መርተው ወደ ቅድስናህ ተራራና ወደ ማደሪያህ ይውሰዱኝ፤›› (መዝ. ፵፪፥፫) በማለት ዘምሯል፡፡ ነቢያት ‹‹ብርሃን›› በማለት የጠሩት ወልደ እግዚአብሔር ክርስቶስ ከሰማያት ወርዶ ሰው ኾኖ ሲያስተምር ‹‹እኔ የዓለም ብርሃን ነኝ፤ የሚከተለኝ የሕይወት ብርሃን ይኾንለታል እንጂ በጨለማ አይመላለስም›› (ዮሐ.፰፥፲፪)፤ እንደዚሁም በተመሳሳይ ምሥጢር ‹‹እውነትንም ታውቃላችሁ፤ እውነትም አርነት ያወጣችኋል፤›› (ዮሐ.፰፥፴፪) በማለት የነቢያቱ ትንቢት በእውነተኛው ብርሃን በእርሱ (በክርስቶስ) መፈጸሙን አረጋግጧል፡፡

እንደዚሁ ነቢዩ ኢሳይያስም፡- ‹‹የዛብሎን ምድርና የንፍታሌም ምድር የባሕር መንገድ፣ በዮርዳኖስ ማዶ የአሕዛብ ገሊላ በጨለማ የተቀመጠው ሕዝብ ታላቅ ብርሃን አየ፤ በሞት አገርና ጥላ ለተቀመጡትም ብርሃን ወጣላቸው፤›› በማለት ተናግሯል (ኢሳ.፱፥፲-፪)፡፡ ይህ ቃለ ትንቢት ይፈጸም ዘንድ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በያገሩ እየተዘዋወረ ድውያነ ሥጋን በተአምራቱ፣ ድውያነ ነፍስን በትምህርቱ እየፈወሰ በኃጢአትና በደዌ ጨለማ ተውጠው ለነበሩ ዅሉ ብርሃን ኾኗቸዋል (ማቴ.፬፥፲፭-፲፰)፡፡

የአጥቢያ ኮከብ መውጣት የሌሊቱን ማለፍ እንደሚያበሥር ዅሉ የነቢያት ትንቢትም ለሐዋርያት ስብከት መንገድ ጠራጊ ነበር፡፡ ነቢያት ‹‹ይወርዳል፤ ይወለዳል›› ብለው በከፈቱት የትንቢት የሐዲስ ኪዳን በር ሐዋርያት ገብተው ወንጌልን ለዓለም ሰበኩበት፤ የክርስቶስን በሥጋ መገለጥ መሰከሩበት፡፡ የዓለም ብርሃን ክርስቶስ ካደረበት አድረው፣ ከዋለበት ውለው በተማሩት ትምህርት፣ ባገኙት ልጅነት ምክንያት ‹‹የዓለም ብርሃን የብርሃን ልጆች›› ተብለው ለመጠራት በቅተዋል (ማቴ.፭፥፲፪፤ ሉቃ.፲፮፥፰)፡፡

ነቢያት በዐረፍተ ዘመን ስለ ተገቱ ትንቢት የተናገሩለትን፣ ሱባዔ የቈጠሩለትን፣ ብርሃን ብለው የጠሩትን ጌታ በዓይነ ሥጋ አላዩትም፡፡ ሐዋርያት ግን ነቢያት የዘሩትን የትንቢት ፍሬ ሰብስበውታል፡፡ ከጨለማው ዓለም ወጥተው፣ ከሥጋዊ ግብር ተለይተው፣ ከባርነት ወደ ልጅነት፣ ከኃጢአት ወደ ስርየት ተመልሰው ወደ ፍጹም ብርሃን ደርሰው የዓለም ብርሃን ክርስቶስ በደሙ ፈሳሽነት ዓለምን እንዳዳነ፣ ዲያብሎስን ድል አድርጎ የቀደመ ልጅነታችንን እንደ መለሰ እስከ ዓለም ዳርቻ ዞረው መስክረዋል፡፡ ለምዕት ዓመታት በግብጽ ምድር በባርነት ተይዘው የኖሩት እስራኤል ዘሥጋ በዓምደ ብርሃን እየተመሩ ወደ ርስት አገራቸው ከነዓን እንደ ገቡ ዅሉ እስራኤል ዘነፍስም በእውነተኛው ብርሃን በክርስቶስ መሪነት ወደ ገነት (መንግሥተ ሰማያት) ለመግባት ችለዋል፡፡

ቅዱስ ዳዊት ‹‹በውኑ ‹ጨለማ ትሸፍነኛለች› ብል ሌሊት በዙሪያዬ ብርሃን ትኾናለች፤ ጨለማ ባንተ ዘንድ አይጨልምምና፤ ሌሊትም እንደ ቀን ታበራለችና›› በማለት እንደ ተናገረው (መዝ. ፻፴፰፥፲፩-፲፪)፣ በአምላካችን ዘንድም ጨለማ የሚባል ነገር ከቶ የለም፡፡ ‹‹ለሰዉ ዅሉ የሚያበራው እውነተኛው ብርሃን ወደ ዓለም ይመጣ ነበር፤ በዓለም ነበረ፡፡ ዓለሙም በእርሱ ኾነ፤ ዓለሙም አላወቀውም … ብርሃን በጨለማ ይበራል፤ ጨለማም አላሸነፈውም፤›› (ዮሐ.፩፥፱-፲፭) ተብሎ በቅዱስ ወንጌል የተመሰከረለት፤ ጨለማ የማያሸንፈው፣ ለዘለዓለሙ የማይጠፋው፣ ተራራ የማይጋርደው፣ የቦታ ርቀት የማይከለክለው እውነተኛው ብርሃን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ዓለም መጥቶ ሕዝብንና አሕዛብን በአንድነት ወደ ድንቅ ብርሃን (ወደ እርሱ) አቅርቧቸዋል፡፡ ሊቁ ቅዱስ ኤፍሬምም ይህንን እውነት መሠረት አድርጎ ‹‹ብርሃን ዘበአማን ዘያበርህ ለኵሉ ሰብእ፤ ለሰው ዅሉ የሚያበራ እውነተኛ ብርሃን›› በማለት የክርስቶስን ብርሃንነት (ዓለምን ከጨለማው ዓለም ነጻ ማውጣቱን) መስክሯል /ውዳሴ ማርያም ዘሰኑይ/፡፡

ቅዱሳን ነቢያት በልቡናቸው ትንቢትን እንደ ዝናር ታጥቀው፣ ከሩቅ በሚመለከቱት ተስፋ አሸብርቀው የብርሃኑን መምጣት ሲጠባበቁ ኖረዋል፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያትም በዚህ ብርሃን ተመርተው ደስ እያላቸው ክርስቶስን በመስበክ በትምህርታቸውና በተአምራታቸው ለጨለማው ዓለምና ለሰው ልጅ ልቡና ወንጌልን አብርተዋል፡፡ ነገር ግን ስለ ብርሃን የተነገረውን የትንቢት ቃል ያልተቀበሉ አይሁድና መሰሎቻቸው በኢየሱስ ክርስቶስ የዓለም ብርሃንነት አላመኑምና በክፋትና በክሕደት ጨለማ ውስጥ ይኖራሉ፡፡ ‹‹ብርሃንም ወደዚህ ዓለም ይመጣ ነበር፤ ሰዎችም ሥራቸው ክፉ ስለ ነበር ከብርሃን ይልቅ ጨለማን ስለ ወደዱ ፍርዱ ይህ ነው፡፡ ሥራው ክፉ የኾነ ዅሉ ብርሃንን ይጠላል፡፡ ሥራው እንዳይገለጥ ወደ ብርሃን አይመጣም፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (ዮሐ. ፫፥፲፱)፡፡

፭. ኖላዊ (ጠባቂ፣ እረኛ)

ኖላዊ ሓላፊነት ለተሰጣቸው ዅሉ ምሳሌ ነው፡፡ የብሉይ ኪዳን መሳፍንት፣ ነገሥታት፣ ነቢያትና ካህናት ኖሎት (እረኞች፣ ጠባቂዎች) ተብለው ተጠርተዋል (ኤር.፳፫፥፩-፬፤ ፳፭፥፴፪-፴፰፤ ሕዝ.፴፬፥፩-፲)፡፡ ነቢያት ዓለሙን ለማዳን ወደዚህ ዓለም የመጣውን መሲሕ ክርስቶስን ከገለጡበት የግብር ስያሜ አንደኛው ‹‹ኖላዊ (ጠባቂ)›› የሚለው ቃል ነው፡፡ መድኀኒታችን ክርስቶስ ጠባቂ እንደሌለው በግ ተቅበዝብዞ የነበረ አዳምን ከነልጆቹ ወደ ቀደመ ክብራቸው መልሷቸዋልና ለግብሩ በሚስማማ ስም ጠርተውታል፡፡ ‹‹እግዚአብሔር እረኛዬ ነው፤ የሚያሳጣኝ የለም፡፡ በለመለመ መስክ፣ በዕረፍት ውኃ ያሰማራኛል፤›› እንዲል (መዝ.፳፪፥፩)፡፡

በብሉይ ኪዳን በነቢያቱ ላይ በማደርና በልዩ ልዩ መንገድ እየተገለጠ ሕዝቡን በረድኤት ሲጠብቅ የነበረው እግዚአብሔር አምላካችን ‹‹ኖላዊሆሙ ለእስራኤል አጽምእ ዘይርዕዮሙ ከመ አባግዐ ዮሴፍ ዘይነብር ላዕለ ኪሩቤል አስተርአየ፤ ዮሴፍን እንደ መንጋ የምትመራ የእስራኤል ጠባቂ ሆይ አድምጥ፤ በኪሩቤል ላይ የምትቀመጥ ተገለጥ፤›› (መዝ.፸፱፥፩) የሚለውን የነቢያቱን ልመና ሰምቶ በሐዲስ ኪዳን ራሱን ለሞት አሳልፎ በመስጠት እኛን በጎቹን ከሞት አድኖ እውነተኛ ቸር ጠባቂአችን መኾኑን አረጋግጦልናል፡፡ እርሱም፡- ‹‹አነ ውእቱ ኖላዊ ኄር ወኖላዊሰ ኄር ይሜጡ ነፍሶ ቤዛ አባግዓሁ፣ ቸር ጠባቂ እኔ ነኝ ቸር ጠባቂ ስለበጎቹ ራሱን አሳልፎ ይሰጣል›› በማለት እውነተኛ ቸር ጠባቂአችን መኾኑን ነግሮናል (ዮሐ.፲፥፲፩)፡፡ የነቢያትን ትንቢት፣ የክርስቶስን ትምህርት የተቀበሉት ቅዱሳን ሐዋርያትም ጌታችንን ‹‹ቸር ጠባቂ፣ የእረኞች አለቃ›› ብለውታል፡፡ ‹‹እንደ በጎች ትቅበዘበዙ ነበርና፤ አሁን ግን ወደ ነፍሳችሁ እረኛና ጠባቂ ተመልሳችኋል፤›› እንዲል (ዕብ.፲፫፥፳፤ ጴጥ.፪፥፳፭)፡፡

፮. መድኃኒት

በብሉይ ኪዳን እግዚአብሔር አምላካችን ‹‹የእስራኤል መድኀኒት›› እየተባለ ይጠራ ነበር (መዝ.፵፫፥፯፤ ኢሳ.፵፫፥፲፩፤ ፵፭፥፳፩)፡፡ በእግዚአብሔር ኀይል እየተመሩ ሕዝበ እስራኤልን ከጠላት ይታደጉ የነበሩ መሳፍንትም ‹‹መድኀኒት›› ተብለው ተጠርተዋል፡፡ በዘመናቸው ሕዝቡን ከጠላት ይታደጉ የነበሩ እነዚያ መሳፍንትና ነገሥታት የአማናዊው መድኀኒት የክርስቶስ ምሳሌዎች ነበሩ፡፡ የብሉይ ኪዳን መሳፍንትና ነገሥታት መድኀኒትነታቸው ለአንድ ወገን ብቻ፣ ይኸውም ከሥጋዊ ጠላት ብቻ ማዳን ነበር፤ በመሳፍንቱና በነገሥታቱ ምሳሌነት፣ በነቢያት ትንቢት የተገለጸው አማናዊው መድኀኒት ጌታችንና አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን ዓለምን ከዘለዓለም ሞት አድኗል፡፡ ስለዚህም ‹‹መድኀኒታችን›› እንለዋለን (ዮሐ.፬፥፵፪)፡፡

የነቢያት ትንቢት መነሻም መድረሻም መድኀኒት ክርስቶስ እንደሚወለድና ዓለምን እንደሚያድን መናገር ነውና ጌታችን የታመመውን ዓለም በሽታ ለማራቅና ከደዌው ለመፈወስ የመጣ መድኀኒተ ዓለም መኾኑን መስክረዋል፡፡ ‹‹ለእናንተ ስለሚሰጠው ጸጋ ትንቢት የተናገሩ ነቢያት ስለዚህ መዳን ተግተው እየፈለጉ መረመሩት›› እንዳለ ቅዱስ ጴጥሮስ (፩ኛጴጥ.፩፥፲)፡፡ ጌታችንም ‹‹ሕመምተኞች እንጂ ጤናሞች ባለመድኃኒት አያስፈልጋቸውም፤›› (ማቴ.፱፥፲፪) በማለት መድኀኒቱም ባለመድኃኒቱም እርሱ መኾኑን ተናግሯል፡፡ የእግዚአብሔር መልአክ ደግሞ ‹‹ዛሬ በዳዊት ከተማ መድኀኒት፣ እርሱም ክርስቶስ ጌታ የኾነ ተወልዶላችኋል፤›› በማለት ክርስቶስ መድኀኒት መኾኑን ሲመሰክር (ሉቃ. ፪፥፲፩)፣ ሳምራውያን ምእመናንንም ‹‹እርሱ ክርስቶስ የዓለም መድኀኒት እንደ ኾነ እናውቃለን›› ሲሉ በክርስቶስ መድኀኒትነት ማመናቸውን ተናግረዋል (ዮሐ.፬፥፵፪)፡፡

በአጠቃላይ የነገረ ድኅነት መነሻው፣ ለቅዱሳን ሐዋርያት ስብከትም መሠረቱ የነቢያት ትንቢት ነው፡፡ ሐዲስ ኪዳንን የብሉይ ኪዳን ነቢያት በትንቢታቸው አስቀድመው አዘጋጁት፤ ሐዋርያት ደግሞ ለበሱት፤ ተጐናጸፉት፡፡ ነገረ ድኅነትን ባዘለ ምሥጢር ‹‹ዐይኖቼ ማዳንህን አይተዋልና ባሪያህን አሰናብተኝ›› እያሉ እነስምዖን የመሰከሩለት፤ ሐዋርያት በስሙ ወንጌልን የሰበኩለት መድኀኒታችን ክርስቶስ በሥጋ ተገልጦ ለደዌ ሥጋ ለደዌ ነፍስ ፈውስን በማደሉ፣ እንደዚሁም የዘለዓለም ሕይወትን ለሰው ልጆች በመስጠቱ ነቢያቱ ‹‹መድኃኒት›› ብለውታል፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምም የወገኖቿን መዳን ለራሷ አድርጋ ‹‹መንፈሴም በአምላኬና በመድኀኒቴ ሐሴት ታደርጋለች፤›› በማለት ልጇ ኢየሱስ ክርስቶስ የዓለም መድኀኒት መኾኑን መስክራለች (ሉቃ.፩፥፵፯)፡፡

የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የእመቤታችን አማላጅነት፣ የነቢያትና የሐዋርያት በረከት አይለየን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ነገረ ድኅነት በትንቢተ ነቢያት (የመጀመሪያ ክፍል)

ታኅሣሥ ፲ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በመ/ር ምሥጢረ ሥላሴ ማናየ

ቅዱሳን ነቢያት ሀብተ ትንቢትን ከእግዚአብሔር የተቀበሉ፣ ፈጣሪያቸውን የተከተሉ፣ በመንፈሰ ረድኤት የተቃኙ እንደ መኾናቸው እግዚአብሔር በሰጣቸው ሀብተ ትንቢት ተመርተው ስለ እግዚአብሔር አዳኝነት መስክረዋል፤ ስለ ሰው ልጅ ድኅነትም አስቀድመው ትንቢት በመናገር የሰው ልጅ የእግዚአብሔርን የማዳን ቀን በተስፋ እንዲጠባበቅ አስተምረዋል፡፡ በትምህርታቸውም እንደ ብረት የጠነከረውን፣ እንደ ዐለት የጠጠረውን፣ በአምልኮ ጣዖትና በገቢረ ኃጢአት የሻከረውን የሰው ልጆችን ልቡና ወደ እግዚአብሔር አቅርበዋል፡፡ ነቢያት መንፈሳዊነትን የተላበሱ፤ በትንቢታቸውና በትምህርታቸው የአሕዛብን ልቡና ያስደነገጡ፤ ዓላውያን ነገሥታትን ያንቀጠቀጡ የእግዚአብሔር መልእክተኞች ናቸው፡፡

በዘመናቸውም አምላክ ከሰማይ ወርዶ (ሰው ኾኖ) ከጨለማ ወደ ብርሃን፣ ከሞት ወደ ሕይወት፣ ከጥፋት ወደ ድኅነት እንዲመልሳቸው እግዚአብሔርን ለምነዋል፤ ሱባዔ እየቈጠሩ፣ ትንቢት እየተናገሩም የተስፋውን ዕለት ሲጠባበቁ ኑረዋል፡፡ ለዚህም ነው ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹እውነት እላችኋለሁ፤ ብዙዎች ነቢያትና ጻድቃን የምታዩትን ሊያዩ ተመኝተው አላዩም፡፡ የምትሰሙትንም ሊሰሙ ተመኝተው አልሰሙም፤›› (ማቴ. ፲፫፥፲፯) በማለት ለደቀ መዛሙርቱ የነገራቸው፡፡ የነቢያቱ የትንቢታቸው ፍጻሜ፣ የልመናቸው መደምደሚያም ነገረ ድኅነት ነው፡፡ በመኾኑም ሰውን ለማዳን ወደ ዓለም የሚመጣውን እግዚአብሔርን በትንቢታቸው በሚከተሉት ምሳሌያት ገልጸውታል፤

፩. እጅ (ክንድ)

እጅ ቢወድቁ ተመርጕዘው ይነሡበታል፡፡ እጅ የወደቀውን ንብረት ከአካል ሳይለይ ለማንሣት፣ የራቀውን ለማቅረብ፣ የቀረበውን ለማራቅ ይችላል፡፡ እግዚአብሔር ወልድም ከባሕርይ አባቱ ከአብ፣ ከባሕርይ ሕይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ ሳይለይ ከእግዚአብሔር ርቆ የነበረውን አዳምን ወደ እርሱ አቅርቦታል፤ ከወደቀበት አንሥቶታል፡፡ ስለዚህም ነው ቅዱሳን ነቢያት እግዚአብሔር ወልድን ‹‹እጅ (ክንድ)›› እያሉ የሚጠሩት፡፡ ‹‹ፈኑ እዴከ እምአርያም አድኅነኒ ወባልሐኒ እማይ ብዙኅ ወእምእዴሆሙ ለደቂቀ ነኪር እለ ከንቶ ነበበ አፉሆሙ ወየማኖሙኒ የማነ ዐመፃ፤ እጅህን ከአርያም ላክ፤ አድነኝም፡፡ ከብዙ ውኆች፣ በአፋቸውም ምናምንን ከሚናገሩ፣ ቀኛቸው የሐሰት ቀኝ ከኾነ ከባዕድ ልጆች አስጥለኝ፤›› እንዲል (መዝ. ፻፵፫፥፯-፰)፡፡ ከዚህ ላይ ነቢዩ ዳዊት ‹‹እጅ›› በማለት የጠራው ከሦስቱ አካላት አንዱን እግዚአብሔር ወልድን ነው፡፡ ‹‹አፋቸው ምናምን የሚናገር፣ ቀኛቸው የሐሰት ቀኝ የኾነው ውኆች›› የሚላቸው ደግሞ ዲያብሎስንና ሠራዊቱ አጋንንትን ነው፡፡ ደቂቀ ነኪር (የባዕድ ልጆች) ማለቱም አጋንንት ከክብራቸው ስለ ተዋረዱ በባሕርያቸው ለሰው ልጆችም ለብርሃናውያን መላእክትም ባዕዳን ናቸውና፡፡

እስራኤል ዘሥጋ በጸናች እጅ፣ በተዘረጋች ክንድ ከግብጽ ባርነት፣ ከፈርዖንና ከሠራዊቱ ግዞት ነጻ መውጣታቸው ነገረ ድኅነትን የሚመለከት ምሥጢር ይዟል፡፡ ‹‹በጸናች እጅ፣ በተዘረጋች ክንድ ይለቃችኋል፤ ከአገሩም አስወጥቶ ይሰዳችኋል›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (ዘፀ. ፮፥፩)፡፡ ከዚህ ላይ ‹‹የጸና እጅ፣ የበረታ ክንድ›› የተባለው ዓለምን በሙሉ ከኃጢአት ባርነት፣ ከዲያብሎስ ቁራኝነት ነጻ ያወጣው ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ክንዱን በመስቀል ዘርግቶ በትረ መስቀሉን አንሥቶ በልዩ ሥልጣኑ ዲያብሎስን የቀጣው፣ ሞትን የሻረው፣ ሲኦልን የበረበረው ኃይለኛውን አስሮ ያለውን ዅሉ የነጠቀው እርሱ ነውና፡፡ ‹‹እሙታን ተንሢኦ ሲኦለ ከይዶ በሞቱ ለሞት ደምሰሶ፤ ከሙታን መካከል ተለይቶ ተነሥቶ፣ ሙስና መቃብርን አጥፍቶ ሞትን በሞቱ አጠፋው (ደመሰሰው)›› እንዲል መጽሐፈ ኪዳን፡፡

መድኀኒታችን ክርስቶስ ‹‹አልቦ ዘይክል በዊአ ቤተ ኀያል ወበርብሮተ ንዋዩ ለእመ ኢቀደመ አሲሮቶ ለኀያል፤ ኃይለኛውን ሳያስር ወደ ኀይለኛው ቤት ገብቶ ገንዘቡን መዝረፍ የሚቻለው የለም›› (ማቴ. ፲፪፥፳፱) በማለት እንደ ተናገረው እርሱም ዲያብሎስን አስሮ በሲኦል ተግዘው ይኖሩ የነበሩ ነፍሳትን ዅሉ ነጻ አውጥቷቸዋል፡፡ አምላካችን ‹‹የጸና እጅ›› የተባለ አምላክነት፣ አለቅነት፣ ጌትነት በአጠቃላይ መለኮታዊ ሥልጣን ገንዘቡ ነውና፡፡ ይህ የጸና እጅ ሰማያትን የዘረጋ፣ ምድርን የመሠረተ፣ ሰውን ለማዳን በመስቀል ላይ የተዘረጋ ኃያል ክንድ ነው፡፡ ዓለም የሚድንበት በእጅ የተመሰለው አካላዊ ቃል ወልደ እግዚአብሔር ሕያው መኾኑን ‹‹የእግዚአብሔር እጅ ከማዳን አላጠረችም፤ ጆሮውም ከመስማት አልደነቆረችም፤›› (ኢሳ. ፶፱፥፩) በማለት ልዑለ ቃል ነቢዩ ኢሳይያስ በትንቢቱ ተናግሯል፡፡ ስለዚህም ነቢያቱ ‹‹እጅህን ላክልን›› እያሉ እግዚአብሔርን ሲማጸኑት ቆይተዋል፡፡ ይህን ብርቱ ክንድ ዓለም እንዳልተረዳውም በትንቢታቸው አስገንዝበዋል፡፡ ነገረ ድኅነት ከብዙዎች አእምሮ የተደበቀ ምሥጢር ነበርና፡፡

ነቢዩ ኢሳይያስ በነቢያት የተነገረውን የነገረ ድኅነት ትንቢት የሰው ልጅ አምኖ እንዳልተቀበለው ሲያስረዳ ‹‹ጌታ ሆይ፣ ነገራችንን ማን ያምነናል? የእግዚብሔርስ ክንድ ለማን ተገልጧል?›› (ኢሳ. ፶፫፥፩) በማለት ተናግሯል፡፡ ጌታችን በሕዝቡ ፊት አምላክነቱን የሚገልጹ ተአምራቱን ቢያደርግም አስራኤል ግን አምላክነቱን አምነው አለመቀበላቸው ለዚህ ማስረጃ ነው (ዮሐ. ፲፪፥፴፮-፵)፡፡ ቅዱስ ዳዊትና ኢሳይያስ እንደ አንድ ልብ መካሪ፣ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ኾነው የሰውን ልጅ ለማዳን ወደዚህ ዓለም የሚመጣውን አምላክ ነገረ ድኅነትን በሚመለከት ምሥጢራዊ ቃል ‹‹እጅ ክንድ›› እያሉ ጠርተውታል፡፡

፪. የመዳን ቀንድ

ቀንድ የሥልጣን፣ የኀይል መገለጫ ነው፡፡ የነቢዩ ሳሙኤል እናት ሐና ‹‹ወተለዓለ ቀርንየ በአምላኪየ ወመድኃኒየ፤ ቀንዴ በአምላኬና በመድኃኒቴ ከፍ ከፍ አለ›› (፩ኛ ሳሙ. ፪፥፩) ማለቷ ለጊዜው ስላገኘችው ክብርና የልጇን የሳሙኤልን ሥልጣን (ነቢይነትና ምስፍና) ስትናገር፤ ፍጻሜው ግን ቀንድ የተባለ ዓለም የዳነበት ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መኾኑን ስታመለክት ነው፡፡ ቅዱሳን ነቢያትም እግዚአብሔር ወልድን ‹‹የመዳን ቀንድ›› ብለውታል፡፡ በመዝሙረ ዳዊትም ከዳዊት ወገን ተወልዶ ዓለምን የሚያድነው ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹ቀንድ›› በሚል ቃል ተጠቅሷል፡፡ ‹‹ወበህየ አበቊል ቀርነ ለዳዊት ወአስተዴሉ ማኅቶተ ለመሲሕየ፤ በዚያም ለዳዊት ቀንድን አበቅላላሁ፡፡ ለቀባሁትም ሰው መብራትን አዘጋጃለሁ፤›› ተብሎ እንድ ተጻፈ (መዝ. ፻፴፩፥፲፯)፡፡

እንስሳት ጠላታቸውን የሚከላከሉት፣ ኀይላቸውንም የሚገልጡት በቀንድ ነው፡፡ እኛ የሰው ልጆችም ከጠላታችን ሰይጣን ውጊያ ራሳችንን የምንከላከለውና ድል የምናደርገው በእርሱ ኀይል ነውና ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹የመዳን ቀንድ›› ተብሎ ተጠርቷል፡፡ ‹‹ብከ ንዎግዖሙ ለሎሙ ፀርነጠላቶቻችንን ሉ በአንተ እንወጋቸዋለን፤›› እንዳለ ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ (መዝ.፵፫፥፭)፡፡ ካህኑ ዘካርያስም በቅዱሳን ነቢያት ‹‹የመዳን ቀንድ›› እየተባለ የተጠራው ክርስቶስ በሥጋ የሚገለጥበት ጊዜ መድረሱን ሲያስረዳ ‹‹አንሥአ ለነ ቀርነ መድኃኒትነ እምቤተ ዳዊት ገብሩ በከመ ነበበ በአፈ ነቢያቲሁ ቅዱሳን እለ እምዓለም፤ ከጥንት ጀምሮ በነበሩት በቅዱሳን ነቢያት አፍ እንደ ተናገረ ከባርያው ከዳዊት ቤት ምንድንበትን ቀንድ አስነሣልን፤›› (ሉቃ.፩፥፷፱) በማለት ተናግሯል፡፡ ‹‹እምቤተ ዳዊት ገብሩ›› ማለቱም ነቢዩ ዳዊት ‹‹ቀንድ›› እያለ ትንቢት የተናገረለት ክርስቶስ የዳዊት ወገን ከኾነችው ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም እንደሚወለድ ሲያመለክት ነው፡፡

፫. የማን (ቀኝ)

ቀኝ የኃይል፣ የሥልጣን፣ የመልካም ነገር ምሳሌ ነው፡፡ የብሉይ ኪዳን መሪዎች ሰዎችን ለአገልግሎት ሲልኳቸው ቀኝ እጃቸውን ዘርግተው ይጨብጧቸው ነበር፡፡ በሥራቸው ዅሉ ከእነርሱ እንደማይለዩ የሚያረጋግጡላቸውም ቀኝ እጃቸውን በመስጠት ነበር፡፡ በዚህ ትውፊት መሠረትም ቅዱሳን ጴጥሮስ፣ ያዕቆብና ዮሐንስ ቅዱስ ጳውሎስን በቀኝ እጃቸው ጨብጠውታል፡፡ ይህንንም ‹‹የተሰጠኝን ጸጋ ዐውቀው አዕማድ የሚሏቸው ያዕቆብና ኬፋ፣ ዮሐንስም እኛ ወደ አሕዛብ፣ እነርሱ ወደ ተገረዙት ይሔዱ ዘንድ ለእኔና ለበርናባስ ቀኝ እጃቸውን ሰጡን፤›› በማለት ቅዱስ ጳውሎስ ገልጦታል (ገላ.፪፥፱)፡፡

ቅዱሳን ነቢያት ዲያብሎስን ከነሠራዊቱ ድል ነስቶ ዓለምን የሚያድነውን፤ ኀያል፣ ጽኑዕ የኾነውን አምላካችንን ክርስቶስን ‹‹ቀኝ›› ብለውታል፡፡ ‹‹የማነ እግዚአብሔር ገብረት ኃይለ የማነ እግዚአብሔር አልዓለተኒ፤ የማነ እግዚአብሔር ገብረት ኃይለ፤ የእግዚአብሔር ቀኝ ኃይልን አደረገች፡፡ የእግዚአብሔር ቀኝ ከፍ ከፍ አደረገችኝ፡፡ የእግዚአብሔር ቀኝ ኃይልን አደረገች፤›› እንዲል (መዝ.፻፲፯፥፲፮)፡፡ ይህም ‹‹የእግዚአብሔር ቀኝ›› የተባለ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በድንቅ ጥበቡ፣ በልዩ ሥልጣኑ አምስት ሺሕ ከአምስት መቶ ዘመን በሲኦል ተጥለው የነበሩ ነፍሳትን ከፍ ከፍ እንዳደረጋቸው (ወደ ገነት እንደመለሳቸው) የሚያስረዳ ምሥጢር አለው፡፡ ቅዱስ ዳዊት የተስፋውን ቃልና የመዳኛውን ቀን መድረስ እየተጠባበቀ ‹‹ወይድኃኑ ፍቁረኒከ አድኅን በየማንከ ወስምዓኒ፤ ወዳጆችህ እንዲድኑ፣ በቀኝህ አድን፤ አድምጠኝም፤›› በማለት ይጸልይ ነበር (መዝ.፶፱፥፭)፡፡

ይቆየን

ከሃያ አምስት በላይ የግብጽ ምእመናን በቦምብ ፍንዳታ ሕይወታቸው ዐለፈ

news

ታኅሣሥ ፫ ቀን ፳፻፱ .

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

በግብጽ ካይሮ ከተማ እሑድ ታኅሣሥ ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ረፋድ ላይ ከቅዱስ ማርቆስ ካቴድራል አጠገብ በሚገኘው የቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ጳውሎስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በደረሰ የቦምብ ፍንዳታ ከሃያ አምስት በላይ የግብጽ ምእመናን ሕይወታቸው ዐለፈ፡፡

ፍንዳታው የደረሰው በሴቶች መቆሚያ በኩል መኾኑን ከግብጽ አካባቢያዊ የመረጃ አውታሮች ለመረዳት ተችሏል፡፡

በጥቃቱ ዐርባ ዘጠኝ ሰዎች መቍሰላቸውንና ከእነዚህ መካከልም አብዛኞቹ ሴቶች መኾናቸውን የግብጽ ጤና ጥበቃ ሚኒስትር አሕመድ ኢማድ ተናግረዋል፡፡ እንደ ጤና ጥበቃ ሚኒስትሩ መግለጫ ከቍስለኞቹ መካከል ሦስቱ አሳሳቢ ደረጃ ላይ ይገኛሉ፡፡

egypt-7

ጕዳቱ ለደረሰባቸውና ሕክምና ላይ ለሚገኙት ቍስለኞች የደም ልገሳ እንዲደርግላቸው በማኅበራዊ ሚድያዎች አማካይነት የግብጽ ሆስፒታሎች ጥሪ ማቅረባቸውም ታውቋል፡፡

በፍንዳታው ምክንያት በግብጻውያን ምእመናን ላይ ለደረሰው ሞትና ጉዳት አገሪቱ የሦስት ቀን ኀዘን እንደምታውጅ የግብጽ ፕሬዚዳንት አብደል ፈታሕ አል ሲሲ አስታውቀዋል፡፡

ለድርጊቱ ሓላፊነቱን የወሰደ አካል ግን እስካሁን ድረስ አልተገኘም፡፡

fun-5

በፍንዳታው ሕይወታቸው ያለፈ ምእመናን ሥርዓተ ቀብርም በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ታዎድሮስ ካልዕ መሪነት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት እና ብዙ ሺሕ የግብጽ ምእመናን በተገኙበት ታኅሣሥ ፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በግብጽ ቅድስት ማርያም እና ቅዱስ አትናቴዎስ ቤተ ክርስቲያን ተፈጽሟል፡፡

ምንጭ፡

Orthodoxy Cognate PAGE – Media Network

http://www.dailynewsegypt.com

http://english.ahram.org.eg

ዘመነ አስተምሕሮ (አስተምህሮ) ካለፈው የቀጠለ

ኅዳር ቀን ፳፻፱ .

፬. መጻጕዕ

ከኅዳር ፳፯ እስከ ታኅሣሥ ፫ ያሉትን ሰባት ቀናት የሚያጠቃልለው አራተኛው የዘመነ አስተምሕሮ ሳምንት ‹‹መጻጕዕ›› ይባላል፡፡ የቃሉ ፍቺ በደዌ ዳኛ፣ በአልጋ ቍራኛ የተያዘ በሽተኛ ማለት ሲኾን ዕለቱ ‹‹መጻጕዕ›› ተብሎ መሰየሙም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዕውር ኾኖ የተወለደውን ጐበዝ ዓይን ያበራበትን ዕለት ለማስታዎስ ነው፡፡ የዕለቱ (እሑድ) መዝሙር ‹‹ይቤሉ እስራኤል ኢርኢነ ወኢሰማዕነ ዘዕውሩ ተወልደ ወተከሥተ አዕይንቲሁ በሰንበት ….፤ ዕውር ኾኖ ተወልዶ ዓይኖቹ በሰንበት የበሩለትን ሰው እስራኤል ‹አላየንም፤ አልሰማንም› አሉ ….›› የሚለው የእስራኤላውያንን በክርስቶስ ተአምር አለማመን የሚገልጸው የቅዱስ ያሬድ ትምህርት ነው፡፡

ምስባኩም ‹‹ደቂቀ ዕጓለ እመሕያው እስከ ማእዜኑ ታከብዱ ልበክሙ ለምንት ታፈቅሩ ከንቶ ወተሐሱ ሐሰተ አእምሩ ከመ ተሰብሐ እግዚአብሔር በጻድቁ፤ እናንት የሰው ልጆች፣ እስከ መቼ ድረስ ልባችሁን ታከብዳላችሁ? ከንቱ ነገርን ለምን ትወዳላችሁ? ሐሰትንም ለምን ትሻላችሁ? እግዚአብሔር በጻድቁ እንደ ተገለጠ ዕወቁ፤›› የሚለው እግዚአብሔር ለጻድቃኑ በሚያደርገው ድንቅ ሥራ ማመን እንደሚገባ የሚያስረዳው የዳዊት መዝሙር ነው /መዝ.፬፥፪-፫/፡፡ ወንጌሉ ደግሞ ዮሐ.፱፥፩ እስከ መጨረሻው ሲኾን ቅዳሴውም ቅዳሴ እግዚእ ነው፡፡ በዚህ ሳምንት መድኀኒታችን የዕውሩን ዓይን ከማብራቱ ባሻገር ሕሙማነ ሥጋን በተአምራቱ፤ ሕሙማነ ነፍስን በትምህርቱ ስለ ማዳኑ የሚያወሳ ቃለ እግዚአብሔር ይቀርባል፡፡

በዓቢይ ጾሙ መጻጉዕ መዝሙሩ፡- ‹‹አምላኩሰ ለአዳም››፤ ምስባኩ፡- ‹‹እግዚአብሔር ይረድኦ ወስተ አራተ ሕማሙ ወይመይጥ ሎቱ ኵሎ ምስካቤሁ እምደዌሁ አንሰ እቤ እግዚኦ ተሣሃለኒ፤ እግዚአብሔር በደዌው አልጋ ሳለ ይረዳዋል፤ መኝታውንም ዅሉ ከበሽታው የተነሣ ይለውጥለታል፡፡ እኔስ ‹አቤቱ ይቅር በለኝ፤ አንተን በድያለሁና ለነፍሴ አስተስርይላት› አልሁ›› /መዝ.፵፥፫-፬/፤ ወንጌሉ፡- ዮሐንስ ፭፥፩-፳፭፤ ቅዳሴው ተመሳሳይ (እግዚእ) ነው፡፡ በዚህ ሳምንት የሚቀርበው ትምህርት ለሠላሳ ስምንት ዓመታት ከአልጋው ጋር ተጣብቆ የኖረው በሽተኛ በክርስቶስ ኃይል ከደዌው ተፈውሶ አልጋውን ተሸክሞ መሔዱንና የክርስቶስን ገባሬ ተአምርነት የሚመለከት ነው፡፡

፭. ደብረ ዘይት

አምስተኛውና የመጨረሻው የዘመነ አስተምሕሮ ሳምንት ‹‹ደብረ ዘይት›› በመባል የሚታወቅ ሲኾን የሚያጠቃልለውም ከታኅሣሥ ፬ – ፮ ያሉትን ሦስት ቀናት ነው፡፡ በዕለቱ (እሑድ) ‹‹ሠርዐ ሰንበተ ለሰብእ ዕረፍተ ለእለ በሰማይ ወለእለ በምድር …፤ እግዚአብሔር በሰማይም በምድርም ለሚኖሩ ፍጡራን ሰንበትን ለዕረፍት ሠራ (ፈጠረ) ….፤›› የሚለው የቅዱስ ያሬድ መዝሙር ይዘመራል፡፡ ‹‹ለነዳያኒሃኒ አጸግቦሙ እክለ ወለካህናቲሃኒ አለብሶሙ ሕይወተ ወጻድቃኒሃኒ ትፍሥሕተ ይትፌሥሑ፤ ባልቴቶቿን እጅግ እባርካቸዋለሁ፤ ድሆቿንም እኽልን አጠግባቸዋለሁ፡፡ ካህናቷንም ደኅንነትን አለብሳቸዋለሁ፡፡ ጻድቃኖቿም እጅግ ደስ ይላቸዋል፤›› የሚለው የዳዊት መዝሙር (ምስባክ) ይሰበካል /መዝ.፻፴፩፥፲፭-፲፮/፡፡ የዕለቱ ወንጌል ሉቃስ ፲፪፥፴፪-፵፩ ሲኾን ቅዳሴው ደግሞ ቅዳሴ አትናቴዎስ ነው፡፡ በዚህ ሳምንት ሰንበት የዕረፍት ዕለት መኾኗን ከሚያስገነዝቡ ትምህርቶች በተጨማሪ የደጋግ አባቶችን መንፈሳዊ ታሪክ፣ የወረሱትን ሰማያዊ ሕይወትና ያገኙትን ዘለዓለማዊ ሐሤት መሠረት በማድረግ እኛ ምእመናንም እንደ አባቶቻችን ለመንግሥተ ሰማያት በሚያበቃ ክርስቲያናዊ ምግባር ጸንተን መኖር እንደሚገባን የሚያተጋ ቃለ እግዚአብሔር ይቀርባል፡፡

በዓቢይ ጾሙ ደብረ ዘይት መዝሙሩ፡- ‹‹እንዘ ይነብር እግዚእነ ውስተ ደብረ ዘይት››፤ ምስባኩ፡- ‹‹እግዚአብሔርሰ ገሃደ ይመጽእ ወአምላክነሂ ኢያረምም እሳት ይነድድ ቅድሜሁ፤ እግዚአብሔር በግልጥ ይመጣል፡፡ አምላካችንም ዝም አይልም፤ እሳት በፊቱ ይነዳል፡፡›› መዝ.፵፱፥፫/፤ ወንጌሉ፡- ማቴዎስ ፳፬፥፩-፴፮፤ ቅዳሴ፡- ተመሳሳይ (አትናቴዎስ) ነው፡፡ በሳምንቱ ጌታችን የምጽአቱን ነገር ለደቀ መዛሙርቱ በደብረ ዘይት ማስተማሩን፣ ዳግም ለፍርድ ሲመጣም ለዅሉም እንደ ሥራው መጠን ዋጋውን የሚከፍለው መኾኑን የሚገልጹ ትምህርቶች ይቀርባሉ፡፡

በአጠቃላይ ከላይ የተጠቀሱት አራቱ የዘመነ አስተምሕሮ ሰንበታት (ቅድስት፣ ምኵራብ፣ መጻጉዕና ደብረ ዘይት) ስያሜአቸው ከዐቢይ ጾም ሰንበታት ጋር ተመሳሳይ ቢኾንም የሚዘመሩት መዝሙራት፣ በቅዳሴ ጊዜ የሚሰበኩ ምስባካትና የሚነበቡ ምንባባት እንደዚሁም የሚቀርቡ ትምህርቶች ግን የተለያዩ ናቸው፡፡ ትምህርቶቹ የተለያዩ ናቸው ስንል የሚነገረው ምሥጢርና ይዘት በወቅታዊ በዓላት ላይ የሚያተኵር መኾኑን ለመግለጽ ነው እንጂ በየትኛውም ጊዜ በቤተ ክርስቲያናችን የሚቀርበው ትምህርት አንዱ የእግዚአብሔር ቃል ብቻ ነው፡፡ ሳምንታቱን በዚህ መልክ የከፋፈለውም ሊቁ ቅዱስ ያሬድ ሲኾን ይህንንም ከመጽሐፈ ድጓው መመልከት ይቻላል /ድጓ ዘአስተምሕሮ/፡፡ የተወደዳችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች! ወቅቱ ሲደርስ የዓቢይ ጾም ሳምንታትን የተመለከተ ሰፋ ያለ ትምህርት ይዘን እንደምንቀርብ ከወዲሁ እናሳውቃለን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጮች፡-

  • መጽሐፈ ግጻዌ፡፡
  • ማኅቶተ ዘመን፣ መምህር በሙሉ አስፋው፤ ፳፻፩ ዓ.ም፣ አዲስ አበባ፡፡
  • ጾምና ምጽዋት፣ ዲያቆን ቃኘው ወልዴ፤ ሐምሌ ፳፻፩ ዓ.ም፣ አዲስ አበባ፡፡
  • ያሬድና ዜማው፣ ሊቀ ካህናት (ርእሰ ደብር) ጥዑመ ልሳን ካሣ፤ ፲፱፻፹፩ ዓ.ም፡፡
  • ጥንታዊ የኢትዮጵያ ሥርዓተ ትምህርት፣ ሊቀ ሥልጣናት ሀብተ ማርያም ወርቅነህ፡፡

ዘመነ አስተምሕሮ (አስተምህሮ) የመጀመሪያ ክፍል

ኅዳር ፳፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

የተወደዳችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች! ኅዳር ፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ባቀረብነው ዝግጅት እንዳስታወስነው በቤተ ክርስቲያናችን የዘመን አከፋፈል መሠረት ከኅዳር ፮ ጀምሮ እስከ ታኅሣሥ ፯ ወይም ፲፫ ቀን ድረስ ያለው ወቅት ዘመነ አስተምሕሮ ይባላል፡፡ ትርጕሙም በሃሌታው ‹ሀ› (‹‹አስተምህሮ›› ተብሎ) ሲጻፍ የቃለ እግዚአብሔር ማስተማሪያ (የትምህርተ ወንጌል) ዘመን ማለት ነው፡፡ ሥርወ ቃሉም ‹‹መሀረ – አስተማረ›› የሚለው የግእዝ ግስ ሲኾን፣ ይኸውም የእግዚአብሔር ቸርነቱ፣ ርኅራኄው፣ ትዕግሥቱና የማዳን ሥራው በቤተ ክርስቲያን በስፋት የሚሰበክበት ጊዜ ነው፡፡ በሐመሩ ‹‹ሐ›› (‹‹አስተምሕሮ›› ተብሎ) ሲጻፍ ደግሞ የምሕረት፣ የይቅርታ ዘመን ማለት ነው፡፡ ሥርወ ቃሉም ‹‹መሐረ – ይቅር አለ›› የሚለው የግእዝ ግስ ነው፡፡ ዘመነ አስተምሕሮ ስለ እግዚአብሔር ቸርነትና ርኅራኄ፤ እርሱ በደላችንን ዅሉ ይቅር እንደሚለን እኛ ምእመናንም እርስበርስ ይቅር መባባል እንደሚገባን ትምህርት የሚሰጥበት ወቅት ነው፡፡

ባለፈው ዝግታችን በዘመነ አስተምሕሮ ውስጥ የሚገኙ ሰንበታት (እሑዶች) አስተምሕሮ፣ ቅድስት፣ ምኵራብ፣ መጻጉዕ እና ደብረ ዘይት በመባል እንደሚጠሩ ጠቅሰን ነበር፡፡ ነገር ግን ከመጀመሪያው ሳምንት ከአስተምሕሮ በስተቀር የአራቱ እሑዶቹ ስያሜ ከዐቢይ ጾም ሰንበታት ጋር ተመሳሳይ በመኾኑ መደናገራቸውን አንዳንድ ምእመናን ገልጸውልናል፡፡ እውነት ነው፤ የሰንበታቱ ስያሜ ከዐቢይ ጾም ሰንበታት ጋር ተመሳሳይ ይኹን እንጂ የሚዘመሩ መዝሙራት፣ በቅዳሴ ጊዜ የሚነበቡ ምንባባትና የሚቀርቡ ትምህርቶች ግን ይለያያሉ፡፡ ልዩነታቸውን ለማነጻጸርና ለመረዳት እንዲያመቸንም በእነዚህ ሰንበታት የሚነገረውን ቃለ እግዚአብሔር ይዘት እንደሚከተለው በአጭሩ እንመለከታለን፤

፩. አስተምሕሮ

የመጀመሪያው የዘመነ አስተምሕሮ ሳምንት ‹‹አስተምሕሮ›› ይባላል፤ ይህም ከኅዳር ፮ – ፲፪ ያሉትን ሰባት ቀናት ያካትታል፡፡ በዕለቱ (እሑድ) የሚቀርበው የቅዱስ ያሬድ መዝሙር ‹‹ኢተዘኪሮ አበሳ ዚአነ ኢኀደገነ ፍጹመ ንማስን ….፤ ኀጢአታችንን አላሰበብንም፤ እንጠፋ ዘንድም ፈጽሞ አልተወንም ….›› የሚለው ሲኾን፣ በተጨማሪም ‹‹ፈጽም ለነ ሠናይተከ እንተ እምኀቤነ ….፤ በአንተ ዘንድ ያለችውን በጎነት ፈጽምልን ….›› የሚለውም እንደ አማራጭ ሊቀርብ ይችላል፡፡ ምስባኩ ‹‹ኢትዝክር ለነ አበሳነ ዘትካት ፍጡነ ይርከበነ ሣህልከ እግዚኦ እስመ ተመንደብነ ፈድፋደ፤ የቀደመውን በደላችንን አታስብብን፡፡ አቤቱ ምሕረትህ በቶሎ ያግኘን፡፡ እጅግ ተቸግረናልና፤›› የሚለው የዳዊት መዝሙር ነው /መዝ.፸፰፥፰/፡፡ ወንጌሉ ማቴዎስ ፮፥፭-፲፮ ሲኾን፣ ቅዳሴውም ቅዳሴ እግዚእ ነው፡፡ በዚህ ሳምንት እግዚአብሔር አምላካችን ከአምስት ሺሕ አምስት መቶ ዓመት የመርገምና የጨለማ ዘመን ዓለምን ማውጣቱ፣ ቸርነቱ፣ ርኅራኄውና ትዕግሥቱ፤ እንደዚሁም ምእመናንን ከሞተ ሥጋ ከሞተ ነፍስ ማውጣቱ ይነገርበታል፡፡

፪. ቅድስት

ከኅዳር ፲፫ – ፲፱ ያሉትን ሰባት ቀናት የሚያካትተው የዘመነ አስተምሕሮ ሁለተኛው ሳምንት ‹‹ቅድስት›› ይባላል፤ ቅድስት የተባለበት ምክንያትም ሰንበትን ለቀደሰ ለልዑል እግዚአብሔር ምስጋና ማቅረብ እንደሚገባ የሚነግርበት ሳምንት መኾኑ ነው፡፡ በዚህ ዕለት (እሑድ) ‹‹ሎቱ ስብሐት ወሎቱ አኰቴት ለዘቀደሳ ለሰንበት ….፤ ሰንበትን ላከበራት ለእርሱ ክብር ምስጋና ይኹን (ይድረሰው፤ ይገባዋል) ….›› የሚለው የቅዱስ ያሬድ መዝሙር ይቀርባል፤ በቅዳሴ ጊዜም ‹‹ኵሎ ዘፈቀደ ገብረ እግዚአብሔር በሰማይኒ ወበምድርኒ በባሕርኒ ወበኵሉ ቀላያት፤ በሰማይና በምድር፣ በባሕርና በጥልቆችም ዅሉ እግዚአብሔር የወደደውን ዅሉ አደረገ፤›› የሚለው ምስባክ ይሰበካል /መዝ.፻፴፬፥፮/፡፡ ወንጌሉ ዮሐንስ ፭፥፲፮-፳፰ ሲኾን ቅዳሴው ደግሞ አትናቴዎስ ነው፡፡ በዚህ ሳምንት ስለ ዕለተ ሰንበት ቅድስትነት እና ሰንበትን ስለቀደሰ ስለ እግዚአብሔር ቅድስና ሰፊ ትምህርት ይቀርባል፡፡

በአንጻሩ በዓቢይ ጾሙ ቅድስት መዝሙሩ፡- ‹‹ግነዩ ለእግዚአብሔር››፤ ምስባኩ፡- ‹‹እግዚአብሔርሰ ሰማያተ ገብረ አሚን ወሠናይት ቅድሜሁ ቅድሳት ወዕበየ ስብሐት ውስተ መቅደሱ፤ እግዚአብሔር ግን ሰማያትን ፈጠረ፡፡ እምነትና በጎነት በፊቱ፣ ቅድስናና የክብር ጋናናነት በመቅደሱ ውስጥ ናቸው፡፡›› /መዝ.፺፭፥፭-፮/፤ ወንጌሉ፡- ማቴዎስ ፮፥፲፮-፳፭፤ ቅዳሴው ደግሞ ኤጲፋንዮስ ነው፡፡ በዚህ ሳምንት የሚነገረው ቃለ እግዚአብሔር ስለ እግዚአብሔር ይቅር ባይነትና ለእርሱ ስለ መገዛት፣ ስለ ቅድስና እና ስለ ክብረ ሰንበት የሚያስረዳ ነው፡፡

 ፫. ምኵራብ

ሦስተኛው የዘመነ አስተምሕሮ ሳምንት ‹‹ምኵራብ›› የሚባል ሲኾን ይህም ከኅዳር ፳ – ፳፮ ያሉትን ሰባት ቀናት የሚያካትት ሳምንት ነው፡፡ በዕለቱ (እሑድ) የሚቀርበው መዝሙር፡- ‹‹አምላክ ፍጹም በህላዌሁ ዘሀሎ እምቅድመ ይትፈጠር ዓለም ….፤ ዓለም ከመፈጠሩ አስቀድሞ የነበረው አምላክ (እግዚአብሔር) በህልውናው (አነዋወሩ) ፍጹም ነው ….››  የሚለው ሲኾን፣ ምስባኩም፡- ‹‹ቅረቡ ኀቤሁ ወያበርህ ለክሙ ወኢይትኀፈር ገጽክሙ ዝንቱ ነዳይ ጸርሐ ወእግዚአብሔር ሰምዖ፤ ወደ እርሱ ቅረቡ፤ ያበራላችሁማል፡፡ ፊታችሁም አያፍርም፡፡ ይህ ችግረኛ ጮኸ፤ እግዚአብሔርም ሰማው፤›› የሚል ነው /መዝ.፴፫፥፭-፮/፡፡ ወንጌሉም ከማቴዎስ ፰፥፳፫ እስከ መጨረሻው ድረስ ነው፡፡ ቅዳሴው ደግሞ እግዚእ፡፡ በዚህ ሳምንት ጌታችን፣ አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምኵራበ አይሁድ ሕዝቡን እየሰበሰበ ማስተማሩ፤ ባሕርና ነፋሳትን መገሠፁ፤ አጋንንትን ከሰዎች ማውጣቱ ይነገራል፡፡

በዓቢይ ጾሙ ምኵራብ መዝሙሩ፡- ‹‹ቦአ ኢየሱስ ምኵራቦሙ ለአይሁድ››፤ ምስባኩ፡- ‹‹እስመ ቅንዐተ ቤትከ በልዐኒ ትዕይርቶሙ ለእለ ይትዔየሩከ ወድቀ ላዕሌየ ወቀፃዕክዋ በጾም ለነፍስየ፤ የቤትህ ቅናት በልቶኛልና፣ የሚሰድቡህ ስድብም በላዬ ወድቋልና፡፡ ሰውነቴን በጾም አደከምኋት፡፡›› /መዝ.፷፰፥፱-፲/፤ ወንጌሉ፡- ዮሐንስ ፪፥፲፪ እስከ ፍጻሜው ሲኾን ቅዳሴው ግን ተመሳሳይ (ቅዳሴ እግዚእ) ነው፡፡ በሳምንቱ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምኵራበ አይሁድ ማስተማሩንና በቤተ መቅደሱ ዓለማዊ ሸቀጥ ይለውጡ የነበሩ ገበያተኞችን ማስወጣቱን የሚመለከት ትምህርት ይቀርባል፡፡

ይቆየን

 

የጽዮን ምርኮ – የመጨረሻ ክፍል

ኅዳር ፳፮ ቀን ፳፻፱ .

በመምህር ብዙነህ ሺበሺ

ታቦተ ጽዮን ከቤተ አሚናዳብ እስከ ዳዊት ከተማ ….

ወደ ታቦተ ጽዮን በተመለከቱ ፸ ቤትሳምሳውያንና ታቦቱን ለመያዝ እጁን በዘረጋ በዖዛ ላይ የእግዚአብሔር ቍጣ ነድዶ ከቀሠፋቸው ‹‹ታቦት (ጽላት) አያስፈልግም!›› የሚሉ ተሐድሶ መናፍቃን የት ይኾን መገኛቸው? ዕድል ፈንታቸው፣ ጽዋ ተርታቸውስ ምን ይኾን? ዖዛ ሙሴንና አሮንን ይቃወሙ የነበሩ መሬት ተከፍታ የዋጠቻቸው የዳታንና አቤሮን፣ ሐዋርያትን የመንፈስ ቅዱስን ስጦታ በገንዘብ ሽጡልኝ በማለት የጠየቃቸው የሰማርያው መሠሪ (ጠንቋይ) ሲሞን፣ በሊቃውንት አባቶች ተወግዘው የተለዩ የአርዮስ፣ ንስጥሮስ፣ አቡሊናርዮስ፣ መቅዶንዮስ ወዘተ ምሳሌ ነው፡፡ እነሱ የማይገባቸውን ሽተው ከዕውቀታቸው በላይ የኾነውን እናውቃለን በማለታቸው በሥጋቸው መቅሠፍት፣ በነፍሳቸውም ሞት እንዳመጡ የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት ላለመስማት ጆሯቸውን በጣታቸው የደፈኑ አራዊተ ምድር ተሐድሶ ነን ባዮች መናፍቃንም አወዳደቃቸው የከፋ ይኾናል፡፡ አርዌ ምድር (እባብ) ሰው ነድፋ አዋቂ ደጋሚ ደግሞባት የተነደፈው እንዳይድን ድጋሙን ላለመስማት አንዱን ጆሮዋን ከምድር ታጣብቃለች፡፡ ቀሪውን በጅራቷ ትደፍናለች /መዝ. ፶፯፥፬-፭፣ አንድምታ ትርጓሜ/፡፡ ስብሐተ እግዚአብሔርን ላለመስማት ጆሮዋን እንደምትደፍን አርዌ ምድር የቤተ ክርስቲያንን የቀና ትምህርት እንዳይሰሙ ተሐድሶ መናፍቃን ጆሮአቸውን በምንፍቅና ትምህርት ደፍነዋል፡፡

ወደ ታሪኩ እንመለስና በዖዛ ስብራት ዳዊት ደነገጠ፤ ታቦተ እግዚአብሔርን ወደ መናገሻ ከተማው ይዞ ይሔድ ዘንድ ስለ ፈራ በአቢዳራ ቤት አኖሩአት፤ የአቢዳራም ቤት ተባረከ፡፡ አቢዳራ የወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ ምሳሌ ነው፡፡ ታቦተ ጽዮንም የእመቤታችን ምሳሌ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ጌታችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹ነያ እምከ፤ እነኋት እናትህ›› ብሎ እመቤታችንን አደራ ከሰጠው ጊዜ ጀምሮ እስከ ዕለተ ዕረፍቷ ድረስ ሲያገለግላት ኖሯል፡፡ ታቦተ ጽዮን የአቢዳራን ቤት እንደ ባረከች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምም የዮሐንስን ቤት ባርካለች፡፡ ‹‹ሐዋርያው ለእጁ በትር ለእግሩ ጫማ የሌለው የቱን ሀብት ነው የባረከችው?›› የሚል ጥያቄ ከተነሣ በእርግጥ ቅዱስ ዮሐንስ የዚህ ዓለም ሀብት ንብረት የለውም፡፡ የጌታችንን መከራ መስቀል በማሰብ ቊፁረ ገጽ ኾኖ (ግንባሩን ቋጥሮ) በኀዘን እንደ ኖረ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ያስተምራሉ፡፡ የቅዱስ ዮሐንስ ሀብት ሀብተ መንፈስ ቅዱስ የኾነው ወንጌልን ማስተማር፣ ነገረ እግዚአብሔርን ማመሥጠር፣ ድውይ መፈወስ፣ ወዘተ. ነው፡፡ ቅዱስ የሐንስ የጻፈው ወንጌል ከሦስቱ ወንጌላት ለየት ያለ ነው፡፡ ሦስቱ ወንጌላት የክርስቶስን የሰውነት ባሕርያት አጕልተው ሲያሳዩ የዮሐንስ ወንጌል ግን የመለኮትን ባሕርይ በጥልቀት ያስረዳል፡፡ በዚህም የተነሣ ወንጌላዊው ‹‹ዮሐንስ ታኦጐሎስ (ነባቤ መለኮት)›› የሚል ስም አግኝቷል፡፡ ስለ መለኮት አምልቶ አስፍቶ የጻፈ ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስን በጸጋ እግዚአብሔር፣ በመንፈሳዊ ዕውቀት ያከበረው፣ የባረከው የእመቤታችን ወደ ቤቱ መግባት ነው፡፡

እመቤታችን በዓይኗ የምታየውን፣ ከመላእክት የተነገራትን በልቧ ጠብቃ ያኖረችውን የልጇን ባሕርየ መለኮት (አምላክነት) ለቅዱስ ዮሐንስ ነግራዋለች /አቡነ ሺኖዳ ሣልሳዊ የመስቀል ጕዞ/፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ከጌታችን እግር ይቀመጥ ስለ ነበር በቅርብ ያየውን ነገረ እግዚአብሔር፣ ከእመቤታችን የተነገረውንም ምሥጢር በሰፊው ጽፏል፤ አስተምሯል፡፡ ከጊዜ እጥረትና ከአገልግሎት ብዛት የተነሣ ያልተጻፉ ምሥጢራትና ተአምራት እንዳሉም ‹‹ኢየሱስም በዚህ መጽሐፍ ያልተጻፈ ሌላ ብዙ ምልክት በደቀ መዛሙርቱ ፊት አደረገ፡፡ ነገር ግን ኢየሱስ እርሱ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ እንደ ኾነ ታምኑ ዘንድ፣ አምናችሁም በስሙ ሕይወት ይኾንላችሁ ዘንድ ይህ ተጽፏል›› በማለት መስክሯል /ዮሐ. ፲፱፥፴-፴፩/፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንም ትውፊት የምትቀበልበት አንደኛው ማስረጃ ይህ ቃል ነው፡፡ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ዶግማ መሠረት የኾነው ይህ ወንጌል ቅዱስ ዮሐንስ እመቤታችንን በመቀበሉ ያገኘው ሀብት ነው፡፡ አዕማድ የተባሉ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እነ ቅዱስ አትናቴዎስ፣ ቅዱስ ቄርሎስ፣ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ኤፍሬም ዘሶርያ፣ ያዕቆብ ዘሥሩግ፣ ባስልዮስ ጐርጐርዮስ (ነባቤ መለኮት)፣ ወዘተ. የድርሰታቸው፣ የትምህርታቸው መሠረት የዮሐንስ ወንጌል ነው፡፡ መናፍቃን የተረቱበት፣ አጋንንት የወደቁበት፣ ቤተ ክርስቲያን የጸናችበት ይህ ወንጌል ነው፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ በእመቤታችን ቃል ኪዳን የሚታመኑ ክርስቲያኖችን ይወክላል፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ወላዲተ አምላክ ብሎ በአማላጅቷ የሚተማመን፣ በቀናች ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት የሚጸና ምእመን በወንጌል ትርጕም ግራ አይጋባም፡፡ ዮሐንስን የባረከች እመቤታችን ምሥጢሩን ትገልጽለታለችና፡፡ የወንጌሉ ትርጕምና ምሥጢር የተደፈነባቸው (የተሰወረባቸው) ተሐድሶ ነን ባዮች መናፍቃን በድንግዝግዝ ጨለማ እየተደናበሩ የሚገኙትና ስተው የሚያስቱት እመቤታችንን ባለመቀበላቸው ነው፡፡ እመቤታችንን በቤቱ ተቀብሎ ቅዱስ ዮሐንስ በብዙ ሀብታተ መንፈስ ቅዱስ እንደ ተባረከ ዛሬም እርሷን እናቴ፣ እመቤቴ ብሎ የሚቀበል በሥጋም በነፍስም ይባረካል፡፡ ምድራዊ ቤቱ በሀብት፤ የእግዚአብሔር መቅደስ የኾነው ሰውነቱም በጸጋ መንፈስ ቅዱስ ይሞላል፡፡ የአቢዳራ ቤት በታቦተ ጽዮን እንደ ተባረከ በሰማ ጊዜ ቅዱስ ዳዊት መንፈሳዊ ቅናት ቀንቷል፡፡ ‹‹ቅንዑ ለእንተ ተዓቢ ጸጋ፤ ለምትበልጠው ጸጋ ቅኑ›› እንዲል፡፡ ቅዱስ ዳዊት በታቦተ እግዚአብሔር ፊት በእግሩ እያሸበሸበ፣ በጣቱ በገና እንደረደረ ሲያመሰግን በንቀት የተመለከተችው ሜልኮል ማኅፀኗ ደርቋል፡፡ ቅዱስ ዳዊት የትሑታን ካህናት፣ መዘምራን በአጠቃላይ የትሑታን ክርስቲያኖች ምሳሌ ሲኾን፣ ሜልኮል ደግሞ የመናፍቃንና የአፅራር ቤተ ክርስቲያን ምሳሌ ናት፡፡

ሜልኮል እስከ ዕለተ ሞቷ መካን ኾና እንደ ቀረች የእመቤታችንን ክብር የሚያቃልሉ መናፍቃንም የመንፈስ ቅዱስ ፍሬን ከማፍራት የመከኑ ናቸው /ገላ. ፭፥፳፪/፡፡ አንድም ሜልኮል ራሳቸውን ከፍ ከፍ የሚያደርጉ ትዕቢተኞች ምሳሌ ናት፡፡ ጌታችን በምሳሌነት የጠቀሰው ፈሪሳዊ ራሱን ጸሎተኛ፣ ሃይማኖተኛ የሚያደርግና ሌላውን የሚንቅ ነበር፡፡ በዚህ ፈሪሳዊ የተናቀው ስለ ኃጢአቱ እያሰበ ወደ ሰማይ ቀና ብሎ ለማየት ያፍር፣ ይሸማቀቅ የነበረው ቀራጭ ድኅነት አግኝቶ ሲመለስ ፈሪሳዊው ግን በነበረው ኀጢአት ላይ የትዕቢት ኀጢአት ጨምሮ እንደ ተመለሰ በቅዱስ ወንጌል ተጽፏል /ሉቃ. ፲፰፥፲-፲፬/፡፡ ‹‹አመ ሜጠ እግዚአብሔር ፄዋ ጽዮን ወኮነ ፍሡሐነ፤ እግዚአብሔር የጽዮንን ምርኮ በመለሰ ጊዜ ደስተኞች ኾንን›› በማለት በደስታ የዘመሩት ቅዱስ ዳዊትና ቤተ እስራኤል በረከት እንዳገኙ ዅሉ እኛ ምእናንም ታቦተ እግዚአብሔር ከመንበረ ክብሩ ወጥቶ በሚከበርበት ዕለተ በዓል በተሰጠን ጸጋ ዘምረን (አመስግነን) በረከት እንድናገኝ እግዚአብሔር ትሑት ልቡና፣ ቅን ሕሊና ይስጠን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፡-

ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ፣ ከኅዳር ፩ – ፲፮ እና ከ፲፮ – ፴ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም፡፡

የጽዮን ምርኮ – ክፍል አራት

ኅዳር ፳፬ ቀን ፳፻፱ .

በመምህር ብዙነህ ሺበሺ

 ለታቦተ ጽዮን ካሣ እንደ ተሰጣት ….

 ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት ‹‹አመ ሜጠ እግዚአብሔር ፄዋ ጽዮን ወኮነ ፍሡሓነ አሜሃ መልአ ፍሥሓ አፉነ ወተሐሥየ ልሳንነ፤ እግዚአብሔር የጽዮንን ምርኮ በመለሰ ጊዜ እጅግ ደስተኞች ኾንን፡፡ በዚያን ጊዜ አፋችን ደስታን አንደበታችንም ሐሤትን ሞላ፤›› /መዝ. ፻፳፭፥፩-፪/ በማለት እንደ ተናገረው በሰማይ በማኅበረ መላእክት፤ በምድር በደቂቀ አዳምና ከሲዖል በወጡ ነፍሳት ዘንድ ትልቅ ደስታ ኾነ፡፡ የጽዮን ምርኮ የተባሉት ለጊዜው ታቦተ ጽዮንን ጨምሮ የአይጥና የእባጭ ወርቆች ሲኾኑ ፍጻሜው ግን የሲዖል ነፍሳት ከዲያብሎስ ምርኮ መመለሳቸውን ያመለክታል፡፡ ታቦተ ጽዮን በምድረ ፍልስጥኤም የኖረችው ሰባት ወራት ነው፡፡ እመቤታችንም በግብጽ በስደት የኖረችው ሰባት መንፈቅ (ሦስት ዓመት ከስድስት ወር) ነው፡፡ ‹‹እስመ ኍልቊ ሳብዕ ፍጹም ውእቱ በኀበ ዕብራውያን፤ ሰባት ቍጥር በዕብራውያን ዘንድ ፍጹም ነውና›› እንዲል፡፡ ጽዮን ሰባት ወር በፍልስጥኤም ኖራ የወርቅ ካሣ ይዛ በድል እንደ ተመለሰች እመቤታችንም ለሰባት መንፈቅ በግብጽ ኖራ ሞተ ሄሮድስን በመልአክ ተበሥራ በደስታ ወደ አገሯ ገሊላ ናዝሬት ተመልሳለች፡፡

ታቦተ ጽዮን ከፍልስጥኤም በሁለት ላሞች በሚጐተት ሠረገላ ተጭና ስትመጣ ሳይገባቸው ሳጥኑን ከፍተው በማየታቸው ከ፭፻ ቤትሳምሳውያን መካከለል ፸ ሰዎች ተቀሥፈዋል፡፡ ዛሬም ቤተ ክርስቲያንን የሚዳፈሩ በደዌ ሥጋ እየተመቱ በነፍሳቸውም ከእግዚአብሔር ጸጋ ምሕረት የራቁ ብዙዎች ናቸው፡፡ እግዚአብሔር ያከበራትን ታቦት በመደፋፈራቸው በሞት እንደ ተቀጡ ቤትሳምሳውያን ዛሬም እግዚአብሔር ባከበራቸው ቅዱሳን ይልቁንም መልዕልተ ፍጡራን መትሕተ ፈጣሪ በኾነችው በእናታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ላይ የድፍረት ቃል የሚሰነዝሩና ጣታቸውን የሚቀስሩ ተሐድሶአውያን መናፍቃንና ተላላኪዎቻቸው ከእግዚአብሔር ምሕረት፣ ቸርነት፤ ከቅዱሳኑም በረከት ርቀው መርገመ ጌባል እየተጐነጩ ይገኛሉ፡፡ በሥጋ ይንቀሳቀሱ እንጂ በነፍሳቸው ሙታን ናቸው ‹‹ሞታ ለነፍስ ርኂቅ እምእግዚአብሔር፤ የነፍስ ሞቷ ከእግዚአብሔር መራቅ ነው›› ተብሎ ተጽፏልና፡፡

ወደ ታቦተ ጸዮን በመመልከታቸው ቤትሳምሳውያን ከተቀሠፉ አማናዊት ጽዮን በኾነችው በእመቤታችን ላይ እባብ ምላሳቸውን የሚያውለበልቡ መናፍቃንማ ዕድል ፈንታቸው ጽዋ ተርታቸው እንዴት የከፋ ይኾን! የአሚናዳብ ልጅ አልዓዛር ታቦተ ጽዮንን እንዲያገለግል እንደ ቀደሰ (እንደ ተመረጠ) በሐዲስ ኪዳንም ቤተ መቅደሱን የሚያገለገሉ በአንብሮተ እድ የተሾሙ ካህናት ናቸው እንጂ ማንም ወደ ታቦተ እግዚአብሔር መቅረብ አይችልም፡፡ ታቦት ወጥቶ በክብረ በዓል ጽላተ ኪዳን ወደ ተሸከሙ ቀሳውስት የሚጠጉ አንዳንድ ሰዎች አሉ፡፡ አስተባባሪዎች እንዲርቁ ቢነግሩአቸውም አይሰሙም፤ እነዚህ ሰዎች ከቤትሳምሳውያን ቅሥፈት መማር አለባቸው እንላለን፡፡ የሚገባውን ክብር በፍርሃትና በፍቅር ካደረግን እግዚአብሔር ደግሞ ያከብረናል፡፡ ነገር ግን በተቃራኒው የምንጓዝ ከኾነ በበረከት ፋንታ መርገምን፣ በሕይወት ፋንታ መቅሠፍትን ሊያደርስብን ይችላልና እንጠንቀቅ፡፡

ታቦተ ጽዮን ከቤተ አሚናዳብ እስከ ዳዊት ከተማ /፩ኛ ሳሙ. ፯፥፩-፪፣ ፪ኛ ሳሙ. ፮፥፩-፳፫/

ታቦተ ጽዮን በኮረብታማው አገር በአሚናዳብ ቤት ለሃያ ዓመት ኖራለች፡፡ ንጉሥ ዳዊት የእግዚአብሔርን ታቦት ያመጣ ዘንድ ሠላሳ ሺሕ ሠራዊት ይዞ ወደ አሚናዳብ ቤት ወጣ፡፡ የአሚናዳብ ልጆች አሕዮና ዖዛ ታቦቱን በአዲስ ሠረገላ ጭነው ሲሔዱም ዳዊትና የእስራኤልም ቤት ዅሉ በቅኔና በበገና፣ በመሰንቆም፣ በከበሮም፣ በነጋሪትና በጸናጽል በእግዚአብሔር ፊት በሙሉ ኀይላቸው ይዘምሩና ያሸበሽቡ ነበር፡፡ ሠረገላውን የሚጐትቱ በሬዎች ይፋንኑ (ይቦርቁ) ነበርና ዖዛ እጁን ዘርግቶ የእግዚአብሔርን ታቦት ያዘ፡፡ ስለ ድፍረቱም እግዚአብሔር በዚያው ቀሠፈው፡፡ ያ ቦታም እግዚአብሔር ዖዛን ሰብሮታልና ‹‹የዖዛ ስብራት›› ተባለ፡፡ ዳዊትም በኪሩቤል ላይ በተቀመጠ በሠራዊት ጌታ በእግዚአብሔር ስም የሚጠራውን ታቦት ወደ ከተማው ይወስድ ዘንድ ስለ ፈራ በጌት ሰው በአቢዳራ ቤት አስቀመጠው፡፡

ታቦተ እግዚአብሔር በቤተ አቢዳራ ለሦስት ወራት ተቀመጠች፤ የአቢዳራም ቤት ተባረከ፡፡ ዳዊትም የአቢዳራ ቤት እንደ ተባረከ በሰማ ጊዜ ታቦተ እግዚአብሔርን ወደ ከተማው ያመጣ ዘንድ ብዙ ሠራዊትና ሌዋውያን ካህናትን አስከትሎ ወደ አቢዳራ ቤት ሔደ፡፡ ዳዊትና የእስራኤልም ቤት ዅሉ ታቦቱን ይዘው ሲመለሱ ስድስት ርምጃ በሔዱ ጊዜ አንድ በሬና ፍሪዳ ይሠዉ፤ ቀንደ መለከትም ይነፉ ነበር፡፡ ዳዊት የበፍታ ኤፉድ ለብሶ ‹‹አመ ሜጠ እግዚአብሔር ጼዋ ጽዮን ወኮነ ፍሡሓነ አሜሃ መልአ ፍሥሓ አፉነ ወተሐሥየ ልሳንነ፡፡ እግዚአብሔር የጽዮንን ምርኮ በመለሰ ጊዜ ደስተኞች ኾንን፡፡ በዚያን ጊዜ አፋችን ደስታን፣ አንደበታችንም ሐሤትን ሞላ፤›› በማለት በታቦተ ጽዮን ፊት በጣቱ በገና እየደረደረ፣ በእግሩ እያሸበሸበ ሲዘምር አይታ ሚስቱ የሳዖል ልጅ ሜልኮል በልቧ ናቀችው፤ አቃለለችው፡፡ በዚህ ምክንያትም ማኅፀኗ ስለ ደረቀ ሜልኮል መካን እንደ ኾነች ሳትወልድ ሞተች፡፡ በዚህ ረጅም ታሪክ ውስጥ የሚገኘውን ተግሣፅ፣ ትምህርትና ምሳሌ ከዚህ ቀጥለን እንመለከታለን፡፡

ታቦተ ጽዮን በኮረብታማው አገር በቤተ አሚናዳብ እንደ ኖረች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምም በተራራማው አገር በቤተ ዘካርያስ ቤት ሦስት ወራት ተቀምጣለች /ሉቃ. ፩፥፴፱፣፶፮/፡፡ ሁለቱ በሬዎች ታቦተ ጽዮን የተቀመጠችበትን ሠረገላ ሲጐትቱ የፋነኑበት (የቦረቁበት) ምክንያት ነቢዩ ኢሳይያስ ‹‹በሬ የገዢውን፣ አህያም የጌታውን ጋጣ አወቀ፤›› /ኢሳ. ፩፥፫/ እንዳለው የእግዚአብሔር የኪዳኑን ታቦት እንደ ተሸከሙ ስላወቁ ደስታቸውን ለመግለጥ ነው፡፡ ጌታችን በቤተልሔም በከብቶች በረት በተወለደ ጊዜ እስትንፋሳቸውን የገበሩለት አምላክነቱን አውቀው ነበር፡፡ ሁለቱ በሬዎች ታቦተ ጽዮንን ተሸክመው ከቤተ አሚናዳብ ወደ ቤተ አቢዳራ እንደ ተጓዙ ዮሴፍና ሰሎሜም የእመቤታችን የስደቷ ተካፋይ ኾነዋል፡፡ ሁለቱ በሬዎች በደስታ እየቦረቁ ሠረገላውን እንደ ጐተቱ ዮሴፍና ሰሎሜም የእመቤታችን የስደቷ አጋር ኾነው ሲሔዱ ሳይጕረመርሙና የስደቱን መከራ ሳይሳቀቁ በፍቅር ኾነው  እመቤታችንን አገልግለዋል፡፡

ዖዛ ታቦተ ጽዮንን በመንካቱ የእግዚአብሔር ጣ በእርሱ ላይ ነደደ፤ ተቀሠፈም፡፡ ዖዛ የእመቤታችን አስከሬን የተቀመጠበትን የአልጋ ሸንኮር በመያዝ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል እጁን በሰይፍ የቀጣው የታውፋንያ ምሳሌ ነው፡፡ አንድም ዖዛ የዮሳ ምሳሌ ነው፡፡ ዖዛ የእግዚአብሔርን ታቦት በመያዙ ተሰብሯል (ተቀሥፏል)፤ ዮሳም እመቤታችንን በማስደንገጡ ድንጋይ ተንተርሶ ቀርቷል (ተቀሥፏል)፡፡ ታሪኩም እንዲህ ነው፤ እመቤታችን ከሄሮድስ ሠራዊት ሸሽታ ዮሴፍን፣ ሰሎሜን እና ዮሳ ወልደ ዮሴፍን አስከትላ የስደት ጕዞዋን ጀመረች፡፡ መሽቶባቸው ከሶርያው ገዥ ከጊጋር ቤት አደሩ፤ በዚያም ዮሳ ታሞ ቀረ፡፡ ‹‹ዘመዶቼ ምን ደርሶባቸው ይኾን?›› ብሎ ወደ መንገድ ቢወጣ ሰይጣን በሰው አምሳል ተገልጦ ‹‹የሄሮድስ ሠራዊት ቀድመው ሔደዋል›› አለው፡፡ ዮሳም በፍጥነት መንገዱን ይዞ በፍጥነት ተከተላቸው፡፡ ደክሟቸው በአንድ ዛፍ ጥላ ሥር አርፈው ባገኛቸው ጊዜ ‹‹እናንተ በሰላም ተቀምጣችኋል፤ ሕፃን በጀርባዋ ያዘለች፣ በክንዷ የታቀፈች ሴት በኢየሩሳሌም አትገኝም፡፡ ሄሮድስ ሕፃናትን አስፈጅቷል፡፡ አሁንም ወደ እናነተ ሠራዊቱን ልኳል›› በማለት እመቤታችንን አስደነገጣት፡፡ ጌታችንም ‹‹ዮሳ አመጣጥህ መልካም ነበር፤ እናቴን አስደንግጠሃታልና በዳግም ምጽአት አስነሥቼ ዋጋህን እስከምሰጥህ ድረስ ይህችን ድንጋይ ተንተርሰህ ተኛ›› ብሎት በዚያው አሳርፎታል፡፡

የዖዛና የዮሳ ታሪክ ተመሳሳይ ነው፡፡ ዖዛ የተቀሠፈው በሬዎቹ ስለሚቦርቁ ታቦተ ጽዮን ከሠረገላው እንዳትወድቅ ለመደገፍ በማሰቡ ነበር፡፡ ዮሳም መልካም ዜና ያመጣ መስሎት ነው እመቤታችንን ያስደነገጣት፡፡ ‹‹ዮሳ ወልደ ዮሴፍ ምንተ ገብረ ኃጢአተ ዘያደነግፀኪ ዜና በይነ ዘአምጽአ ግብተ፤ የዮሴፍ ልጅ ዮሳ ምን በደል ሠራ የሚያስደነግጥሽ ዜናን በድንገት በማምጣቱ እንጂ›› እንዳለ ደራሲ፡፡ ስለዚህ ‹‹መክፈልት ሲሹ መቅሠፍት›› እንዲሉ መልካም ያደረግን እየመሰለን ስሕተት ልንሠራ ስለምንችል የምንሠራውን ሥራ ቆም ብለን ልንመረምር ይገባናል፡፡ ጌታችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም መልካም የሠሩ እየመሰላቸው የእግዚአብሔርን ሕግ ስለሚጥሱ አይሁድ ‹‹ይመስሎ ከመ ዘመሥዋዕተ ያበውእ ለእግዚአብሔር፤ ለእግዚአብሔር መሥዋዕት የሚያቀርብ ይመስለዋል›› በማለት ተናግሯል /ዮሐ. ፲፮፥፪/፡፡

ይቆየን