የደቡብ ማእከላት የአንድነት ጉባኤ አካሔዱ፡፡

ሰኔ ፲ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በሐዋሳ ማእከል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን በሐዋሳ ማእከል አዘጋጅነት በደቡብ ማስተባበሪያ ሥር ያሉት የዘጠኝ ማእከላት ሥራ አስፈጻሚዎችና አባላት ከሰኔ ፫-፭ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ድረስ በሐዋሳ ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን የግቢ ጉባኤ አዳራሽ የልምድ ልውውጥና የአንድነት ጉባኤ አካሔዱ፡፡

በዕለቱ የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጸሐፊ አቶ ተስፋዬ ቢኾነኝ፣ እንዲሁም የማኅበረ ቅዱሳን ሥራ አመራር አባል አቶ ፋንታኹን ዋቄ የተገኙ ሲኾን፣ በመርሐ ግብሩ መክፈቻ ላይም የነቃህ ኹን /ራእ.፫፥፪/ በሚል ኃይለ ቃል ወቅታዊውን የቤተ ክርስቲያን አገልግሎትና ሓላፊነትን መሠረት ያደረገ ትምህርተ ወንጌል በዲያቆን ስንታየሁ ጂሶ ተሰጥቷል፡፡ በጉባኤውም ፺ የየማእከላት ሥራ አስፈጻሚ ጉባኤና የሐዋሳ ማእከል አባላት ተሳትፈዋል፡፡

በጉባኤው ሁለተኛ ቀን የቤተ ክርስቲያንን ኹለንተናዊ አገልግሎት ለመደገፍ የማኅበረ ቅዱሳንን ድርሻ የሚያመለክት ሥልጠና በማኅበሩ ዋና ጸሐፊ አቶ ተስፋዬ ቢኾነኝ የተሰጠ ሲኾን፣ በልምድ ልውውጡ መርሐ ግብርም መልካም አርአያነት ያላቸው ማእከላትና ንዑሳን ክፍሎች የልምድ ተሞክሯቸውን ለጉባኤው ተሳታፊዎች አካፍለዋል፡፡

እንደዚሁም በደቡብ ማእከላት ማስተባበሪያ ጽ/ቤት ሓላፊ በመ/ር ዘሪሁን ከበደ የዘጠኙም ማእከላት የአራት ዓመት የማኅበረ ቅዱሳን ስልታዊ ዕቅድ አፈጻጸም ማጠቃለያ የቀረበ ሲኾን፣ በተጨማሪም በጉባኤው ፫ኛ ቀን ውሎ፣ Living the Orthodx Life in the Era of Globalization and Secular Humanism፤ ኦርቶዶክሳዊ ሕይወት በዘመነ ሉላዊነትና ዓለማዊነት በሚል ርእስ በአቶ ፈንታሁን ዋቄ የግማሽ ቀን ሥልጠና ተሰጥቷል፡፡

በመጨረሻም የደቡብ ማእከላት ማስተባበሪያ ጽ/ቤት ሓላፊ ይህ ጉባኤ ለየማእከላቱ አገልግሎት መነሣሣት የሚኖረውን አስተዋጽኦ ከገለጹና የ፳፻፱ ዓ.ም ተመሳሳይ ጉባኤ አዘጋጅ ወላይታ ዶ ማእከል እንዲሆን ከተወሰነ በኋላ ሰኔ ፭ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ከምሽቱ ፭ ሰዓት የአንድነት ጉባኤው ተፈጽሟል፡፡