ራስን የመግዛት ጥበብ


ጥር 29/2004 ዓ.ም

በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ

 

ቅዱስ ዮሐንስ ዘደማስቆ “ፍልስፍና ማለት ጥበብን ማፍቀር ማለት ነው፤ ጥበብ ደግሞ እግዚአብሔር ነው፤ ስለዚህም ፍልስፍና ማለት እግዚአብሔርን ማፍቀር ማለት ነው”ብሎ ያስተምራል፡፡ እኛም በበኩላችን እግዚአብሔር ፍቅር ነው፤ ሰውም በእግዚአብሔር አርዓያና አምሳል የተፈጠረ ስለሆነ ሰው ፍቅር የሚገዛው ፍጥረት ሆነ እንላለን፡፡ አንድ ጸሐፊ ስለ ሰው ተፈጥሮ ሲያስተምር፡- “እግዚአብሔር ሰውን ከፍቅር አፈር አበጀው፡፡ ስለዚህም ሰው ፍቅር የሚገዛው ፍጥረት ሆነ፤ ስለዚህም ሰው ፍቅር ሲያጣ እንደ በድን ሬሳ ሲቆጠር በፍቅር ውስጥ ካለ ሕያው ነው፡፡ ሕይወቱም እግዚአብሔር ነው፤ እግዚአብሔርም ፍቅር ነው፡፡” ስለዚህም ክርስቲያናዊ ፍልስፍና ፍቅርን መሠረት ያደርጋል፡፡ ነገር ግን ለፍልስፍና ትምህርታችን መንደርደሪያ የሚሆነን ፍቅር የሆነውን ተፈጥሮአችንን በሚገባ ማወቃችንና መረዳታችን ነው፡፡

ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ በእግዚአብሔር መልክና ምሳሌ የተፈጠረውን ሰውን ትንሹ ዓለም ይለዋል፡፡ እንዲህም ያለበት ምክንያት ሰማያዊና ምድራዊ ተፈጥሮ ያለው በመሆኑ ነው፡፡ ረቂቅ በሆነችው የነፍስ ተፈጥሮው በኩል ረቂቃን ከሆኑ መናፍስት ጋር አኗኗሩን ሲያደርግ፤ ግዙፍ በሆነችው ሥጋዊ ተፈጥሮው በኩል ደግሞ በምድር ፍጥረታት ላይ ገዢ ሆኖ ጠቅሟቸውም ተጠቅሞባቸውም ይኖራል፡፡ ስለዚህም ነው ሰው በሁለት ዓለማት እኩል የሚኖር ፍጥረት ነው መባሉ፡፡ ወይም ሰው የሁለት አካላት ውሕደት ውጤት ነው፡፡ ነፍስ የራሱዋ የሆነ አካል ያላት ስትሆን በዚህ ተፈጥሮዋ መላእክትን ትመስላቸዋለች፣ እንደ ምግባሩዋ ከቅዱሳን ወይም ከርኩሳን መናፍስት ጋር ኅብረትን ትፈጥራለች፡፡ በነፍስ ሕያው ሆና የምትኖር ሥጋችንም ከዚህ ዓለም ጋር ተመጋግባና ተግባብታ ለመኖር የሚረዳት የራሱዋ የሆነ አካላዊ ተፈጥሮ ያላት ናት፡፡ መንፈስ የሆነው እግዚአብሔር ለመንፈሳዊያንና(በእርሱ ዘንድ ረቂቃን አይደሉም) ለምድራዊያን ፍጥረታት ሕይወትን ሰጥቶ እንደሚያኖራቸው እንዲሁ ነፍስም ለሥጋ ሕይወትን ሰጥታ ታኖራታለች፡፡ በዚህም ተፈጥሮአችን አምላክን እንመስለዋለን፡፡ “ሠዓሊ ቀለማትን አዋሕዶ የራሱን መልክ እንዲሥል እንዲሁ እግዚአብሔር ነፍስና ሥጋን በማዋሐድ የራሱን መልክ በመሳል ሰው አድርጎ ፈጠረው፡፡”(ቅዱስ ኤፍሬም)

 

ነፍስ ከሥጋ ተፈጥሮአዋ ሳትለይ ከመንፈሳዊያን ፍጥረታት ጋር ኅብረትን መፍጠር ይቻላታል፡፡ ሥጋም ከነፍስ ሳትለይ ነፍስ ሕይወት ሆኗት ለራሷ ሕልውና ጠቃሚ የሆኑትን ተግባራት በምድር ላይ ታከናውናለች፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር አምላክ እንዲህ አድርጎ ሰውን ከፈጠረው በኋላ የሕይወት እስትንፋስ የሆነውን መንፈስ ቅዱስን በአፍንጫው እፍ አለበት፡፡ (አክሲማሮስ ገጽ.156) መንፈስ ቅዱስም ለነፍሳችን እውነተኛ እውቀትን በመግለጥ፤ ነፍስ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ሥጋዋን እንድትመራት ይረዳታል፡፡ እግዚአብሔር ሰውን እንዲህ አድርጎ ፈጠረው፡፡ ስለዚህም ሰው ማለት ሥጋው ለነፍሱ፣ ነፍሱም ለመንፈስ ቅዱስ የሚገዙለት ፍጥረት ማለት ነው፡፡

 

አንድ ሰው ይልቁኑ አንድ ክርስቲያን ይህ ሰብአዊ ተዋቅሮውን ካወቀ እግዚአብሔር እርሱን ለምን ዓላማ እንደፈጠረው ይረዳል፡፡ ስለዚህም ነው የትምህርት መጀመሪያው ራስን ማወቅ ነው ብለው ቅዱሳን አባቶች ማስተማራቸው፡፡ ለምሳሌ ቅዱስ ኤፍሬም “ማንነትህን የማታውቅ ከሆነ የፈጣሪህን ቃል መስማት እንዴት ይቻልሃል?”ሲል፣ ቅዱስ ባሲልዮስ ዘቂሳርያ ደግሞ “ከትምህርቶች ሁሉ የሚልቀው ትምህርት ራሰን ማወቅ ነው፡፡ አንድ ሰው ራሱን ከአወቀ እግዚአብሔርን ያውቀዋል፡፡ እግዚአብሔርን ከአወቀ ደግሞ እግዚአብሔር አምላኩን ይመስላል” ብሎ ያስተማረው፡፡ ራስን ማወቅ የመንፈሳዊ ሕይወታችን መሠረት ነው፡፡

 

ቅዱሳን አባቶቻችን ራስን የማወቅ ጥበብን በሦስት የእውቀት እርከኖች ከፋፍለው ያስቀምጡታል፡፡ የመጀመሪያው እርከን ማንነትን መረዳት ነው፡፡ ይህ እርከን ተፈጥሮአዊ መዋቅርን የመረዳት እርከን (carnal stage) ተብሎ ይታወቃል፡፡ ያም ማለት የራስን ተፈጥሮዊ ጠባይ ማወቅ ማለት ነው፡፡ ሰው ራሱን ካወቀ ራሱን ለመግዛትና እንደ ፈጠሪው ፈቃድ ለመመላለስ መሠረት ይጥላል፡፡ ራሳችንን ካወቅን በኋላ የሚቀጥለው የእውቀት እርከን መንፈሳዊያኑንና ምድራዊያኑን የስሜት ሕዋሳቶቻችንን ተጠቅመን አካባቢያችንን መረዳት ነው፡፡ በዚህ እርከን ውስጥ ስንገኝ በዙሪያችን ያሉትን ረቂቃን መናፍስትንና ግዙፋን ፍጥረታትን ወደ መረዳትና ከእነርሱ ጋር ግንኙትን ወደ መጀመር እንመጣለን፡፡ ይህም የለብዎ እርከን(sensual stage) ይባላል፡፡  ሦስተኛውና የመጨረሻው እርከን መንፈሳዊያን ሆነን የምንመላለስበት እርከን ሲሆን መንፈሳዊ እርከን ተብሎ ይታወቃል (spiritual stage)፡፡ ይህ የቅዱሳን መላእክትንና የአጋንንትን ንግግር የምንለይበትና በመንፈስ ቅዱስ መሪነት የምንመላለስበት የእውቀት ወይም የቅድስና እርከን ነው፡፡ ይህን እርከን ቅዱስ ጳውሎስ “መንፈሳዊ ሰው ግን ሁሉን ይመረምራል ራሱ ግን በማንም አይመረመርም፡፡ እንዲያስተምረው የጌታን ልብ ማን አውቆት ነው እኛ ግን የክርስቶስ ልብ አለን”በማለት ይተነትነዋል፡፡(1ቆሮ.2፡15-16)

 

አንድ ሰው መንፈሳዊ ነው የምንለውም እነዚህ የእውቀት እርከኖችን አልፎ የመንፈስ ቅዱስን መልእክት ማዳመጥና መለየት ወደሚችልበት እርከን ሲሸጋገር ነው፡፡ ይህን ለማስረዳት ቅዱሳን “በክርስቶስ ያመነ አንድ ሰው አውቃለሁ፤ ዘመኑ ከዐሥራ አራት ዓመት በፊት ነው፤ ነገር ግን በሥጋው ይሁን በነፍሱ እንጃ፤ እግዚአብሔር ያውቃል ያ ሰው እስከ ሦስተኛው ሰማይ ድረስ ነጥቀው ወሰዱት” (2ቆሮ.12፡2) ብሎ ቅዱስ ጳውሎስ ያስተማረውን ይጠቀማሉ፡፡ እንደ ቅዱሳኑ አስተምህሮ ሦስቱ ሰማያት የተባሉት ቅዱሱ ያለፈባፋቸውን ሁለቱን የእውቀት እርከኖችንና በስተመጨረሻ የደረሰበትን የእርሱን የእውቀት ከፍታን ነው፡፡ በዚህ የእውቀት እርከን ውስጥ የሚገኝ ቅዱስ በዚህ ምድር ሳለ የትንሣኤን ሕይወት ጣዕም መቅመስ ይጀምራል፡፡ ይህም ማለት  ከአምላክ ጋር፣ ከቅዱሳን መላእክትና ከቅዱሳን ነፍሳት ጋር ለመነጋገር የበቃ ይሆናል፣ የአጋንንትንም ምክርና አሳብ ይለያል፣ በሰው ልቡና የሚመላለሰውን ክፉም ይሁን በጎ አሳብ ማወቅና መረዳት ይችላል፣ መጪውን ያውቃል፡፡ እነኝህን ሁሉ ግን የምናገኘው በመንፈስ ቅዱስ አጋዥነት ነው፡፡

 

ነፍስ ለሥጋ ብርሃኗ እንደሆነች ለነፍስም ብርሃኗ መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ ያለ መንፈስ ቅዱስ ረቂቁንና መንፈሳዊውን ዓለም መረዳት አይቻለንም፡፡ በዚህም ላይ ጨምረን ነፍሳችንን ከኃጢአት ንጹሕ ማድረግ ይጠበቅብናል፤ ያለበለዚያ እውር ድንብራቸውን እንደሚመላለሱ ወገኖች እንሆናለን፡፡ ይህን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “እውነት እውነት እላችኋለሁ ሙታን የእግዚአብሔርን ልጅ ድምፅ የሚሰሙበት ሰዓት ይመጣል እርሱም አሁን ነው” ብሎ ይገልጸዋል፡፡ (ዮሐ.5፥25) ወንድሜ ሆይ በዚህ ቦታ ሙታን ያላቸው ነፍሳቸው የተለየቻቸውንና ወደ መቃብር የወረዱትን ወገኖችን ነውን ? ስለሰማያዊው አኗኗራቸው ፈጽመው የማያቁትን አይደለምን ? ይህ ኃይለ ቃል ምን አልባት ግልጽ ላይሆን ይችላል፤ በማቴዎስ ወንጌል ላይ ጌታችን እርሱን ለሚከተል ደቀመዝሙር የተናገረውን እስቲ እናስተውለው፤ “ኢየሱስም፡- ተከተለኝ ሙታናቸውን እንዲቀብሩ ሙታንን ተዋቸው አለው”(ማቴ.8፥22) ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እነዚህ በቁም ሳሉ ሙታን እንደሆኑ አሳወቀው፡፡ የሞተ ሰው በዚህ ዓለም ምን ይፈጸም ምን አንዳች የሚያውቀው እንደሌለ እንዲሁ እነዚህም ወገኖችም ለሰማያዊው ዓለም እንደምውት ናቸውና ስለሰማያዊ አኗኗራቸው የሚያቁት አንዳች ነገር የላቸውም፡፡ ነገር ግን ሕያዋን እንደተባሉት በሁለቱም ዓለማት ታውረው ይኖሩ ነበር፡፡ በዚህም ምክንያት ጌታችን ሙታን አላቸው እንጂ በሥጋማ መሰሎቻቸውን ሊቀብሩ ተፍ ተፍ እያሉ እኮ ነው!

 

ቅዱሳን “አካሔዳቸውን ከእግዚአብሔር ጋር አደረጉ” ሲባልም ምድራዊ አኗኗራቸውን ትተው ከረቂቃኑ ፍጥረታት ጋር ኖሩ ማለት እኮ አይደለም፡፡ ሄኖክ አካሔዱን ከእግዚአብሔር ጋር አደረገ ሲባል አኗኗሩን ከምድራዊው አኗኗር ለየ ማለት ሳይሆን ሁለቱንም ዓለማት በአግባቡ ኖረባቸው ሲለን ነው፡፡ እርሱ በዚህ ምድር ቤተሰብ መሥርቶ ልጆችንም ወልዶ ይኖር ነበር፡፡ በኋላም አምላኩ ወደ ብሔረ ሕያዋን ወሰደው፡፡ ኖኅ አካሄዱን ከእግዚአብሔር ጋር አደረገ የተባለለት ቅዱስ ነው፡፡ በምድራዊ ሕይወቱም በቅድስና ተመላለሰ፡፡ አብርሃም፣ ይስሐቅ፣ ያዕቆብ በእግዚአብሔር ዘንድ ሕያዋን የተባሉ ቅዱሳን ናቸው (ማቴ.22፥31-32)፡፡ ይህም የሚያሳየው በረቂቁም በግዙፉም ዓለም እኩል ሕያዋን ሆነው ይኖሩ እንደነበር ነው፡፡

 

በእዚህ የእውቀት እርከን ውስጥ ያሉ ቅዱሳን ሕይወት ምን እንደሚመስል ሶርያዊ ቅዱስ ዮሴፍ (ባለራእይው ዮሴፍም ይባላል) እንዲህ ይገልጸዋል፡- “መንፈስ ቅዱስ በእኛ ሰውነት ውስጥ ሥራ መሥራቱን የምንረዳው አእምሮአችን ፍጹም ብሩህ በሆነ የማስተዋል ብርሃን ሲሞላ ነው፡፡ በዚያ ጊዜ በልባችን ጠፈር ላይ የሰንፔር ድንጋይን የመሰለ ሰማይ ተዘርግቶ ከልባችን ጠፈር ልዩ ልዩ ኅብረ ቀለማት ያሉዋቸው ብርሃናት (እውቀቶች) ሲፍለቀለቁ ይታየናል፡፡ እንደነዚህ ዓይነት ማራኪ የሆኑ ብርሃናት በልቡናችን የሚፍለቀለቁት ሥላሴ በልቡናችን ውስጥ የባሕርይ የሆነውን ብርሃን ሲያበራልን ነው፡፡ በሥላሴ ብርሃን እገዛ የሚኖረን እውቀት ፍጥረታዊውን ዓለም በጥልቀት እንድናውቀውና እንድንረዳው የሚያደርገን ሲሆን ከዚህ አልፈን መንፈሳዊውን ዓለም በጥልቀት እንድናውቀው ያበቃናል፡፡ በመቀጠልም ስለ እግዚአብሔር ቅን ፍርድና መግቦት ወደ ማወቅ እንመጣለን፡፡

 

በዚህ መልክ ከፍ ከፍ በማለት ከክርስቶስ የክብሩ ብርሃን ተካፋዮች ለመሆን እንበቃለን፡፡ ከዚህ ቅዱስና ግሩም ከሆነው እይታ ስንደርስ እጅግ ውብ አድርጎ በፈጠራቸው ዓለማት በእጅጉ እንደነቃለን፡፡ ከእነርሱ የምናገኘው ማስተዋል እጅግ ታላቅ ነው፡፡ በዚህ ድንቅ በሆነ የእውቀት ከፍታ ውስጥ ስንገኝ ስለ ሁለቱ ዓለማት ያለን እውቀት እንደ ጅረት ውኃ ከአንደበታችን ሞልቶ ይፈሳል፡፡ የሚመጣውን ዓለም በዚህ ዓለም ሳለን ማጣጣም እንጀምራለን፡፡ እጅግ ውብ የሆነውን የመላእክትን ማስተዋል ገንዘባችን እናደርጋለን፡፡ ደስታቸውን፣ ምስጋናቸውን፣ ክብራቸውን፣ ዝማሬአቸውንና ቅኔአቸውን እንሰማለን፡፡ መላእክትን ከእነ ማእረጋቸውና ከእነ ክብራቸው እንመለከታቸዋለን፣ እርስ በእርሳቸው  ያላቸውንም አንድነት እንረዳለን፣ ቅዱሳን ነፍሳትን ለመመልከት እንበቃለን፣ ገነትን ማየት፣ ከሕይወት ዛፍ መመገብን (መላእክት የሚመግቡትን የፍቅር ማዕድ ማለቱ ነው)፣ ከቅዱሳን ነፍሳትና መላእክት ጋር መነጋገርና ከዚህም ባለፈ ልዩ ልዩ በረከቶችን ለማግኘት የበቃህ እንሆናለን፡፡” ወደዚህ የቅድስና ወይም የእውቀት ከፍታ ለመወጣጣት ግን አስቀድመን እንደጻፍንላችሁ የራስን ማንነትን ማወቅ በእጅጉ ያስፈልጋል፡፡

 

ከላይ ነፍሳችን በሁለቱም ዓለማት አኩል ተሳትፎ እንዳላት ተመለክተናል፡፡ ይህች ረቂቅ የሆነች ተፈጥሮአችን ሥራዎቹዋን የምታጠናቅርበት አካል አላት፡፡ ይህን ረቂቅ አካል እኛ አእምሮ ብለን እንጠራዋለን፡፡ ይህች ነፍስ ሁለት ወገን የሆኑ የስሜት ሕዋሳት ሲኖሩዋት አንደኛው ወገን ረቂቁን ዓለም የምናስተውልበት ሲሆን ሁለተኛው ወገን ግን ግዙፉዋን ዓለም የምንረዳበት ነው፡፡ ነፍስ ረቂቁን ዓለም እና ግዙፉን ዓለም በምትረዳባቸው የስሜት ሕዋሳት በኩል መረጃዎችን ረቂቅ ወደሆነው የአእምሮዋ ክፍል ታስገባለች፡፡ አእምሮም በስሜት ሕዋሳቱ በኩል ያገኛቸውን  ጠቃሚ መረጃዎች ወደ ውስጠኛው የአእምሮ ክፍሉ አስገብቶ ያኖራቸዋል፡፡

 

እንደ ቅዱሳን አባቶቻችን አስተምህሮ አእምሮአችን ሁለት ክፍሎች አሉት፡፡ አንደኛው ልዩ ልዩ አሳቦችን የሚያኖርበት ላይኛው የአእምሮአችን ክፍል እንለዋለን፡፡ ሌላኛው ክፍል ደግሞ አእምሮአችን በላይኛው የአእምሮ ክፍላችን ከሚመላለሱት ዐሳቦች ይጠቅሙኛል ያላቸውን ዐሳቦች የሚያኖርበት ክፍል ነው፡፡ አንድ ዐሳብ ወደ ታችኛው የአእምሮ ክፍላችን ከመግባቱ በፊት በላይኛው የአእምሮአችን ክፍል ረዘም ያሉ ሒደቶችን ያሳልፋል፡፡ እነዚህ ሒደቶች አንድን ሰው ከስህተት ጠብቀው በሰውም በእግዚአብሔርም ዘንድ መልካም ሆኖ እንዲመላለስ ይረዱታል፡፡

 

ሰው ሁለት ወገን ከሆኑት የስሜት ሕዋሳቱ ከመንፈሳዊው ዓለምና ከግዙፉ ዓለም መረጃን ወደ ላይኛው የአእምሮአችን ክፍል ያስገባል፡፡ አእምሮም ለሁለቱ አካላት ማለትም ለነፍስም ለሥጋም የሚጠቅም መስለው ወደ ታዩት ይሳባል ወይም ይረዳቸው ዘንድ ወደ እነርሱ ያዘነብላል፡፡ ይህ ዝንባሌ አጥብቆ መሻት(passion) ይባላል፡፡ አእምሮአችን በአንድ ነገር በመሳቡ ብቻ ዐሳቡን ወደ ተግባር ይመልሰዋል ማለት ግን አይደለም፡፡ ነገር ግን ልክ በካሜራ ምስልን እንደምናስቀር እንዲሁ ለበለጠ መረዳት የተሳበበትን ነገር ምስል በውስጡ ያስቀረዋል፡፡ ይህ ምስልን በልቡና ውስጥ ማስቀመጥ “ምናብ” (imagination) ተብሎ እንጠራዋለን፡፡ በምናብ መልክ በአእምሮአችን ውስጥ ያስቀመጠውን ዐሳብ አእምሮአችን ደግሞ ደጋግሞ ጠቀሜታውንና ጉዳቱን እንዲሁም እውነተኝነቱን ይመረምራል፤ ያሰላስለዋል፡፡ በዚህም አንድ አቋምን ወደ መያዝ ይመጣል፡፡ ይህ ወደ አንዱ ማድላት አቋም (opinion) ይባላል፡፡ ከዚህም በኋላ አእምሮአችን ዐሳቡ ለሰብእናችን የሚጠቅም ሆኖ ሲያገኘው ሊተገብረው ፍላጎት ያድርበታል፡፡ ይህ ፍላጎቱ ፈቃድ (will) ይባላል፡፡ በመጨረሻም ወደ ትግበራ ይመጣል፡፡

 

አእምሮአችን ወደ ተግባር ሊመልሰው የመረጠውንም ዐሳብ ለአተገባበር  እንዲመች ወደ ውስጠኛው የአእምሮአችን ክፍል ያስገባዋል፡፡ ከዚህ በኋላ ነው እግዚአብሔር ወደ ተግባር ለማምጣት በፈቀድነው ፈቃዳችን የሚፈርድብን ወይም የሚባርከን፡፡ ለምሳሌ ንጉሥ ዳዊት ለእግዚአብሔር የቃል ኪዳኗ ታቦት መቅደስ ለመሥራት አሰበ፡፡ ዐስቦም አልቀረም ወደ ተግባር ለመግባት ነቢዩ ናታንን አማከረው፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር ዳዊት ቤቱን እንዲሠራለት ፈቃዱ አልነበረም፤ ቢሆንም ቅን ስለሆነው ዐሳቡ እግዚአብሔር ባረከው እንዲህም አለው “እግዚአብሔር ቤት እንደምትሠራለት ይነግርሃል፤ እሠራለታለሁ ብለሃልና፡፡ ዕድሜህም በተፈጸመ ጊዜ ከወገብህ የሚወጣውን ዘርህን ከአንተ በኋላ አስነሣለሁ፤ መንግሥቱንም አዘጋጃለሁ፡፡ እርሱ ለስሜ ቤትን ይሠራል ዙፋኑን ለዘለዓለም አጸናለሁ” ብሎ ባረከው፡፡ (2ሳሙ.7፡) ይህ ከእርሱ ወገን ክርስቶስ እንዲወለድ የሚያሳይ ዘለዓለማዊ በረከት ነበር፡፡ ምክንያቱም ልጁ ሰሎሞን ለዘለዓለም ነግሦ አላየነውምና፡፡ ለዘለዓለም በዳዊት ዙፋን ላይ የነገሠው ከዳዊት ወገን ከሆነች ከቅድስት ድንግል ማርያም የተወለደው ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ (ሉቃ.1፡31) ክፉን ዐሳብ ዐስቦ እርሱን ለመተግበር ፈቃዱ ያለው ሰው ምንም እንኳ ድንጊቱን በተግባር አይፈጽመው እንጂ ልክ ድርጊቱን እንደፈጸመው ተደርጎ ይፈረድበታል፡፡ እንዲህም ስለሆነ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ወደ ሴት ያየ የተመኛትም ያን ጊዜ በልቡ አመነዝሮአል” ብሎ አስተማረን፡፡(ማቴ.5፡28)

 

ከላይ የዘረዘርናቸውን ሒደቶች የሚፈጸሙት በኅሊናችን መሣሪያነት ነው፡፡ ኅሊናችን ውስጥ እውነትን ከሐሰት የምንለይበት ሚዛን አለ፡፡ እርሱም እግዚአብሔር አምላክ አስቀድሞ በኅሊናችን ያኖረው ሕጉ ነው፡፡ ስለዚህ ነገር ቅዱስ ጳውሎስ ሲያስረዳ “… አሕዛብ ሕግ ባይኖራቸው እንኳ … ኅሊናቸው ሲመሰክርላቸው ኅሊናቸው እርስ በእርስ ሲካሰስ ወይም ሲያመካኝ በልባቸው የተጻፈውን የሕግን ሥራ ያሳያሉ፡፡”(ሮሜ.2፡15) ብሎናል፡፡ ስለዚህም በሁለቱ ወገን የስሜት ሕዋሳቶቻችን ወደ አእምሮአችን የሚገቡ ዐሳቦች ሁሉ እኛን በደለኞች አያሰኙንም፡፡ ነገር ግን እነርሱን በአእምሮአችን ውስጥ አልምተን ወደ መተግበር ፈቃድ ስንመጣ ፍርዱ የዛን ሰዓት በእኛ ላይ ይፈጸማል፡፡

 

ዲያብሎስ ክፉ ዐሳቦችን ከእኛ የመነጩ አድርጎ በአእምሮአችን ውስጥ ሊዘራብን ይችላል፡፡ በዚህ ጊዜ ስጋት ሊፈጠርብን ይችላል፡፡ ነገር ግን ከእርሱ የመነጨውን ክፉ ዐሳብ በጽኑ በመቃወም የእግዚአብሔር ወገን ከሆኑት ቅዱሳን መላእክት ጋር ልንወግን ይገባናል፡፡ ይህን ትምህርት የምንቋቸው ባሕታዊው ዮሐንስ የሚባለው ሶርያዊ ቅዱስ በዚህ ጉዳይ ላይ የጻፈልንን ድንቅ የሆነ ጽሑፍ በመመልከት ይሆናል ፡፡ እንዲህ ይለናል፡- “በልቡናህ የሚመላለሱትን ዐሳቦችን በጥንቃቄ ተከታተላቸው፡፡ ክፉ ዐሳብ በልቡናህ ዘልቆ ቢገባ አትረበሽ ይህ ዐሳብ ከአእምሮህ የመነጨ እንዳልሆነ ከአእምሮህ በላይ ያለውን የሚውቅ ጌታህ ይረዳዋል፡፡ እርሱ የሚመለከተው ጥልቅ ከሆነው የአእምሮህ ክፍል በመነጨ ክፉ ዐሳብ ደስተኛ የሆንክ እንደሆነ ነው፡፡ የሚጠሉ ክፉ ዐሳቦች በላይኛው የአእምሮህ ክፍል ሊመላለሱ ይችላሉ፡፡

 

ቢሆንም እግዚአብሔር የሚመረምረው የተጠሉ ክፉ ዐሳቦችን ለይቶ ማስወገድ የሚችለውን ጥልቁን የአእምሮአችንን ክፍል ነው፡፡ በላይኛው የአእምሮአችን ክፍል በሚመላለሱት በተጠሉ ክፉ ዐሳቦች የተነሣ እግዚአብሔር በእኛ ላይ አይፈርድብንም፡፡ ነገር ግን ከጥልቁ  የአእምሮአችን ክፍል የሚመነጩ የተጠሉ ዐሳቦች ስውር በሆኑ እጆቹ የማስወገድ ችሎታው ካለው  እእምሮ ክፍል የሚመነጩ ከሆኑ ግን ፍርድ ይጠብቀናል፡፡ ከጥልቁ የአእምሮችን ክፍል አመንጭተን ለምናመላልሳቸው ክፉ ዐሳቦች እግዚአብሔር በእኛ ላይ ከመፍረድ አይመለስም፡፡ በላይኛው የአእምሮአችን ክፍል የሚመላለሰው ዐሳብም ወደ ውስጠኛው የአእምሮአችን ክፍል እንዳይገባ መከላከል ስንችል ወደ ውስጥ እንዲገባ ከፈቅድንለት እግዚአብሔር ፍርዱን ከዚህ የተነሣ ይሰጣል፡፡ እንዳውም ክፉ ዐሳብ በውስጥህ ጎጆውን ቢሠራና ብዙ ቀንም በአእምሮህ ቢሰነብት፣ ከእዛም አልፎ ወደ ውስጠኛው ክፍል ቢገባ፣ ነገር ግን ውስጠኛው የአእምሮው ክፍል ያለማቋረጥ ላለመቀበል የሚሟገተውና ከአንተም ትእዛዝ የማይወጣ ከሆነ፣ አትረበሽ ይህ ክፉ የሆነው አሳብ ተነቅሎ መወገዱ አይቀርም፡፡ በዚህም ከእግዚአበሔር ዘንድ የምትቀበለው አንዳች ፍርድ የለም፡፡ ከዚህ ይልቅ ከጥልቁ አእምሮህ የመነጨው መልካሙ ዐስተሳሰብህ ከእግዚአብሔር አምላክህ ዘንድ ታላቅ ዋጋን ያሰጥሃል፡፡ ክፉ ዐስተሳሰብን የሚቃወም የለመደ አእምሮንም ገንዘብህ ታደርጋለህ፡፡”

 

እንግዲህ እግዚአብሔር አምላክ እንዴት እጹብና ድንቅ አድርጎ እንደፈጠረን እናስተውል፡፡ ነገሮችን በአግባቡ እንድናከናውን እግዚአብሔር በአእምሮአችን ውስጥ ልዩ የሆነ ሥርዐትን ዘርግቶልናል፡፡ በእነዚህም የአእምሮ ሥርዐታት አምላክንና ሰውን ሳንበድል ፍቅርን አንግሠናት በዚህ ዓለም በአግባቡ ያለስህተት መመላለስን በሚመጣው ዓለም ከቅዱሳን ጋር የርስቱ ወራሾች ለመሆን እንበቃለን፡፡ እግዚአብሔር ይህን በመረዳት ወደ ተግባር መልሰነው ለመመላለስ ማስተዋል ያድለን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

kahinatSeltena

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች የንስሐ አባቶች ሴሚናር ተካሔደ

በ ዲ/ን  ኅሩይ ባየ

kahinatSeltenaበማኅበረ ቅዱሳን አዘጋጅነት ከጥር 16-18 ቀን 2004 ዓ.ም ድረስ  የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች የንስሐ አባቶች ሴሚናር   በማኅበረ ቅዱሳን ዋናው ማእከል  ተካሔደ ፡፡

 

በማኅበረ ቅዱሳን የሀገር ውስጥ ማዕከላት ግቢ ጉባኤያት ማደራጃና ማስተባበሪያ ዋና ክፍል ሓላፊ የሆኑት ዲያቆን አንዱአምላክ ይበልጣል እንደገለጡት የንስሐ አባቶች በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚገኙ ተማሪዎችን ዘመኑን የዋጀ ትምህርት እንዲያስተምሩና አባታዊ ተልእኳቸውን እንዲወጡ ሴሚናሩ እንደሚያግዛቸው አብራርተዋል፡፡ በተጨማሪም በሥልጠናው ላይ የተገኙ ካህናት ከተለያዩ ቦታ የመጡ በመሆናቸው በአንድ የሥልጠና ቦታ ተገኝተው ልምዳቸውን እንዲለዋወጡና እንዲመካከሩ ለማድረግ ታስቦ የተዘጋጀ ሴሚናር መሆኑን ገልጠዋል፡፡

ከደብረ ታቦር፣ መቀሌ፣ ሽሬ፣ ደሴ፣ ደብረ ማርቆስ፣ ወሊሶ፣ አሰበ ተፈሪ፣ ጋምቤላ፣ ድሬዳዋ፣ ሐዋሳ፣ ፍቼ፣ ባሕርዳር፣ ሚዛንተፈሪ፣ ወላይታ ሶዶ፣ ጅማ፣ መቱ፣ ሰቆጣ፣ ሎጊያ፣ ዲላ፣ ደብረ ብርሃን እና ከአዲስ አበባ የተገኙ 53 ካህናት በሴሚናሩ ተሳትፈዋል፡፡

የሴሚናሩ መርሐ ግብር እንደሚያመለክተው ለተከታታይ 3 ቀናት “የቤተ ክርስቲያን ወቅታዊ ሁኔታ ከተልእኮዋ አንጻር፣ የቤተ ክርስቲያንን ተልእኮ በማስፈጸም ረገድ የንስሐ አባቶች ሚና ምን መሆን እንዳለበት፣ የግብጽ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አባቶች ተሞክሮ የንስሐ ልጆቻቸውን ከመጠበቅ አንጻር ያላቸው ተልእኮ እንዲፋጠን ለማድረግ፣ ሉላዊነት እና ዓለማዊነት፣ መንፈሳዊ የምክር አገልግሎት ከሌሎች የምክር ዐይነቶች የሚለይበትን ጠባይ ምን እንደሆነ፣ የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች መንፈሳዊ ዕድገት ለቤተ ክርስቲያን ሁለንተናዊ እድገት ያለው ሚና፣ እና ማኅበረ ቅዱሳን በግቢ ጉባኤያት ያለው አገልግሎት የሚሉ ዐበይት ጉዳዮች በተያዘላቸው ጊዜ ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡

ሴሚናሩ በተጀመረበት ዕለት ካህናቱ የሕዝብ መሪ ከመሆናቸው አንጻር እንዲህ ዐይነቱ የውይይት መርሐ ግብር እጅግ ጠቃሚና አስፈላጊ መሆኑን ተሳታፊዎች ገልጠዋል፡፡ “አንድ በግ ከሚመራቸው አንድ መቶ አናብስት ይልቅ አንድ አንበሳ የሚመራቸውን አንድ መቶ በጎችን እፈራለሁ” እንደሚባለው፡፡ ጌታ በወንጌል በጎቼን ጠብቅ፣ ጠቦቶቼን ጠብቅ፣ ግልግሎቼን ጠብቅ ብሎ አደራ የሰጠው ለካህናቱ በመሆኑ የጠባቂነት አደራቸውን እንዲወጡ ሴሚናሩ አስገንዝቧል፡፡ ካህናቱ የልጆቻቸውን ሥነ ልቡና ከመረዳት አኳያ ተፈላጊውን ክብካቤ የሚያደርጉበትን መንገድ ማሰብ እንዳለባቸው ሴሚናሩን ያቀረቡት ሊቃውንት አብራርተዋል፡፡

ለሦስት ተከታታይ ዕለታት የዘለቀው ሴሚናር በብሔራዊ ሙዚየም ጉብኝት ከተከናወነ በኋላ ተጠናቅቋል፡፡

dsc01723

የ2004 የከተራ በዓል አከባበር ከዓድባራቱ እሰከ ጃንሜዳ፡፡

ጥር 11/2004ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

በቤተ ክርስቲያናችን ሥርዓት መሠረት ዐበይት በዓላት ተብለው ከሚጠቀሱት መካከል የጥምቀት በዓል አንዱ ነው፡፡ይህንም በዓል ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በእደ ዮሐንስ፤ በማእከለ ዮርዳኖስ የተጠመቀበትን  ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በየዓመቱ ከዋዜማው ከጥር 10 ጀምሮ በደመቀ ሁኔታ በማክበር ላይ ትገኛለች፡፡ ለእኛ አብነት ይሆነን ዘንድ፤ የእዳ ደብዳቤያችንን እንደ ገል ቀጥቅጦ እንደ ሰም አቅልጦ በደላችንን ይደመስስ ዘንድ ጌታ በዮርዳኖስ ወንዝ ተጠመቀ፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ይህንን መሠረት በማረድግ በየአብያተ ክርስቲያናቱ የሚገኙ ታቦታት በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ፣ በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ በካህናትና ዲያቆናት፤ እንዲሁም በሰንበት ት/ቤቶች መዘምራንና ምእመናን በዝማሬ በመታጀብ በአቅራቢያቸው ወደሚገኘው ታቦት ማደሪያ በማምራት ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ ወንዝ በመሔድ በዮሐንስ እጅ ለመጠመቅ ማምራቱን ያበሥራሉ፡፡ ‹‹ያን ጊዜም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከገሊላ ናዝሬት መጣ ዮሐንስም በዮርዳኖሰ ወንዝ አጠመቀው›› እንዲል፡፡/ማቴ.3፡1/

 

dsc01723

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን መሥራቿን መድኀኔዓለም ክርስቶስን ለዓለም የምትሰብክበት፣ ከእርሱም ያገኘችውን፣ ይህም ዓለም እንደሚሰጠው ያልሆነውን፣ የእግዚአብሔር ልጅነት፣ ሰላም፣ ፍቅርና ትሕትና ለዓለሙ ትሰብክበታለች፡፡ እንዲሁም ለአገራችን በጎ ገጽታን በመፍጠር ረገድ ከተለያዩ አገራት የሚመጡ ጎብኚዎች ተደንቀው የሚያዩትና አንዳንዶች ልባችውን ለእውነት ክፍት ያደረጉ የሚያምኑበት በመስተንግዶው የሚደመሙበት በመሆኑ ሃይማኖታዊ በዓሉን በልዩ ትኩረት ታከብራለች፡፡

 

ለዚህ በዓል አከባበር ቤተ ክርስቲያን ቅድመ ዝግጅቶችን በማድረግ ታቦታት በሰላም ወጥተው dsc01724በሰላም እንዲመለሱ ጉልህ ሚናዋን ትወጣለች፡፡ በዚህ መሠረት  በየአጥቢያው የሚገኙ ወጣቶች ከክብረ በዓሉ ቀደም ብሎ ለሓላፊነት በመሰብሰብ ቅዱሳት ሥዕላትን በታቦታት ማረፊያዎች በማዘጋጀት፣ በተለያዩ ኅብረ ቀለማት ያሸበረቁ ጨርቆችን /ባነሮችን/፤ የኢትዮጵያ ባንዲራን በየአብያተ ክርስቲያናቱ አደባባዮች በመስቀል፣ የቤተ ክርስቲያናትን ቅጥርና አስፋልት በማጽዳት፤ለታቦት ክብርን በመስጠት ምንጣፎችን በማንጠፍ በዓሉን ያደምቁታል፡፡

 

‹‹ያሰባሰበንና ያነሳሳን እግዚአብሔር ነው፡፡ በራሳችን ያደረግነው አንዳችም ነገር የለም፡፡ ይህንን ክብረ በዓል ከዐራት ዓመታት ወዲህ ነው በዚህ ሁኔታ በማክበር ላይ የምንገኘው፡፡ በየወሩ ከእያንዳንዱ አባል ዐሥር ዐሥር ብር በማዋጣት፤ ከምእመናን በመጠየቅ፤ እንዲሁም በጎ አድራጊ ምእመናንን በማነጋገር የገንዘብ ድጋፍ  በማድረግ እናሰባስባለን፡፡ ባገኘነው ገንዘብ የኢትዮጵያ ባንዲራን፤ የተለያዩ ኅብረቀለማት ያላቸው ጨርቆችን በchurchesማዘጋጀት፤ ምንጣፎችን በመግዛት  በቤተ ክርስቲያን ልጅነታችን የበኩላችን እንድንወጣ ከበረከቱ ተሳታፊ እንድንሆን እያገለገልን እንገኛለን›› በማለት ስሜቱን ያካፈለን ከመንበረ ልዑል ቅዱስ ማርቆስና  የቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያናት አጥቢያ፤ የስድስት ኪሎ አካባቢ ወጣቶች መካከል አንዱ ወንድም ነው፡፡ በየአጥቢያው ተዘዋውረን የበዓሉን ቅድመ ዝግጅት ለመቃኘት በሞከርንበት ወቅት ያገኘናቸው ወጣቶች የመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ድንግል ማርያም ገዳም አጥቢያ ወጣቶች፤ የቅድስት ማርያም ቤዛዊት ዓለም ማኅበር አባላት፤የዐራት ኪሎ አካባቢ ወጣቶች ቤተ ክርስቲያኒቱንና አደባባዮችን በማስጌጥ ሥራ ላይ ተጠምደዋል፡፡ ስለ ዝግጅቱም የተሰማቸውን ሲገልጹ  ነበር፡፡ በተጨማሪም ‹‹ከፖሊስ አባላት ጋር በመቀናጀት ቅድመ ዝግጅቶችን በማድረግና በመወያየት  አስፈላጊውን ጥበቃ ለማድረግ ተዘጋጅተናል፡፡›› በማለት የገለጹ ሲሆን ባስተላለፉት መልእክትም ወጣቶች የእነሱን አርአያነት በመከተል ቤተ ክርስቲያን ከእነሱ የምትጠብቀውን አገልግሎት እንዲሰጡ እንዲሁም እምነታቸውን አጥብቀው እንዲይዙ ግዴታቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል፡፡

‹‹ኀዲጎ ተስዐ ወተስዐተ ነገደ››
ምእመናን ከየቤታቸው ለበዓሉ በሚገባው ልብስ አሸብረቀው ወጥተዋል፡፡ እናቶቻችን ከየአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናቱ የሚሰሙትን የሊቃውንት አባቶቻችን ወረብ ተከትልው፣ የታቦታቱን መውጣት በመጠባበቅ እልልታቸውን ያሰማሉ፡፡ የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶችም ዝግጅቶቻቸውን አጠናቅዋል፣ የዝማሬ ልብሳቸውን ለብሰዋል፡፡ የሻይ የእረፍት ሰዓታቸውን በመጠቀም ከየመሥሪያ ቤታቸው በር ላይ የታቦታትን ማለፍ በእነርሱም መባረክን ዐይናቸው ተስፋ እያደረገች ታቦታቱ የሚመጡበትን አቅጣጫ ያማትራሉ፡፡

begena04
የማኅበረ ቅዱሳን መዘምራንም ለወትሮው በሚታወቁበት፤ እኅቶች በሙሉ ነጭ ልብስ ወንድሞችም በነጭ ልብስና በቀይ ጃኖ ደምቀው የመንግሥተ ሰማያት ሙሽራ መስለዋል፡፡ ዘንድሮ ግን ሁሉንም ያስደመመ ነገር ይዘው ቀርበዋል፡፡ በርካታ ምእምናንን ዐይናቸውን ማመን እንዳልቻሉ ያስታውቃሉ፡፡ ‹‹በውኑ ይሄን ያህል በገና ደርዳሪ አለን?›› የሚሉ ይመስላል፡፡ አንዳንዶቹም በደስታ ፊታቸው እያበራ በተመሰጦ ‹‹እመቤቴ በምልጃሽ መድኀኒቴ ነሽ›› በሚለው መዝሙር ከበገና ደርዳሪዎቹ ጋር ወላዲተ አምላክን ያመሰግናል፤ ይማጸናል፡፡ ቁጥራቸው ወደ 150 የሚጠጋ የቅዱስ ዳዊት የበገና ቤተሰብ አባላት በገናችውን ወድረው ለዝማሬ ማየት በእውነት ልብን በሐሴት ይሞላል፡፡ ዐይንን ሳይነቅሉ ዐሳብን ሣይከፍሉ ለመከታተል ለመዘመርም ያስገድዳል፡፡ በማኅበረ ቅዱሳን የአቡነ ጎርጎርዮስ ትምህርትና ሥልጠና ማእከልን በርቱ ቀጥሉበት ያስብላል፡፡

ከሰዓት በኋላ በነበረው መርሐ ግብር በተለይም በጃንሜዳ ከየአድባራቱ ዐሥራ ሦስት ታቦታት በአንድነት የሚገኙበት በመሆኑ ሕዝቡን ለመባረክ የተገኙት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ፕሬዚዳንት የዓለም ሃይማኖቶች ለሰላም የክብር ፕሬዚዳንት ከብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ጋር በመሆን፤ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ልብሰ ተክህኖ ለብሰው፤ በመዘምራንና ምእመናን በመታጀብ ጉዞ የተጀመረ ሲሆን አመሻሽ ላይ ጃን ሜዳ ሊደርሱ ችለዋል፡፡ የየሰንበት ት/ቤቶቹ መዘምራን፤ የማኅበረ ቅዱሳን መዝሙር ክፍል አባላት ያሬዳዊ ዜማ እየዘመሩ፤ ምእመናን በእልልታና በሸብሸባ ታቦታቱን በማጀብ በዓሉን አድምቀውታል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ከጋዜጠኞች ለቀረበ ጥያቄ ዕለቱን በማስመልከት በሰጡት መግለጫ ‹‹የዛሬው በዓላችን በሃይማኖታችን ውስጥ የእግዚአብሔርን ጸጋና በረከት የምናገኝበት፤ ሁላችንም በእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ የምንወለድበት፤ ልጅነት የምናገኝበት በዓል ነው፡፡›› በማለት  ገልጸዋል፡፡

በዓሉን በተመለከተ ያነጋገርናቸውና ከፈረንሳይ ሀገር የመጡት ቱሪስት በዓሉን በመገረም እየተከታተሉ ‹‹ወደ ኢትዮጵያ የመጣሁት ለመጀመሪያ ጊዜ ነው፡፡ የራሺያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ተከታይ ነኝ፡፡ ኢትዮጵያውያን በጣም የተለያችሁ ናችሁ ማለት ይቻላል ፡፡ እንደዚህ ዓይነት የበዓል አከባበር ዐይቼ አላውቅም፡፡ በጣም አስደሳችና ታላቅ በዓል ነው፡፡ ሕዝቡ በእልልታና በዝማሬ፣ በሽብሸባና በጭብጨባ የሚያደርጉት እንቅስቃሴ ፍጹም አስደሳች ነው፡፡›› በማለት ገልጸዋል፡፡

በሰሜን አሜሪካ የኦሃዮ ስቴት ኮሎምበስ ከተማ የደብረ ሰላም ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ የሆኑት ቀሲስ ያሬድ ገ/መድኅን  dsc05178ከበዓሉ ተሳታፊዎች መካከል አንዱ የነበሩ ሲሆን ከረጅም ጊዜ በኋላ በሀገራቸው ማክበር በመቻላቸው መደሰታቸውን፤ ወጣቶች ለታቦታቱ ምንጣፍ በማንጠፍ የሚያደርጉት ጥረት እንዳስደነቃቸው የገለጹ ሲሆን፤ በውጭ ሀገር የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ምእመናን  የሚያደርጉት ጥረት በተመለከተ ‹‹እኛ እምነታችንን ለዓለም የምናስተዋውቅበት ጊዜ እየደረሰ ነው፡፡ በውጭው ዓለም አብያተ ክርስቲያናት መተከላቸው፣ በዓላትን በጋራ ማክበራችን የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን ለዓለም ሕዝብ ማስተዋወቅ የጀመርንበት ወቅት እንደሆነ ያሳያል፡፡ እግዚአብሔር ከፈቀደ እነሱም ተጠምቀው የማይመለሱበት፤ የቤተ ክርስቲያን ልጆች የማይሆኑበት ምክንያት አይኖርም ›› በማለት ወደፊት ብዙ መሠራት እንዳለበት ገልጸዋል፡፡

በበዓሉ ላይ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ከውጭ ሀገር በዓሉን ለመከታተል የመጡ እንግዶችና ቱሪስቶች የተገኙ ሲሆን  የዓመቱ ተረኛ የሆነው የመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን መዘምራን ዕለቱን በማስመልከት ያሬዳዊ ዝማሬ ‹‹ተሰአልከ እግዚኦ ምደረከ ሃሌ ሉያ ወረደ ወልድ እም ሰማያት ውስተ ምጥማቃት በፍስሐ ወበሰላም›› በማለት አቅርበዋል፡፡ በብፁዕ ሊቀ ጳጳስ አቡነ ገሪማ ሰፋ ያለ  ቃለ እግዚአብሔር  ተሰጥቷል፡፡ በመጨረሻም በብፁዕ አቡነ ጳውሎስ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ተሰጥቶ ታቦታቱ ወደ ተዘጋጀላቸው ማረፊያ ቦታ ገብተዋል፡፡  

ወስብሐት ለእግዚአብሔር
p1180004

ሁለቱ የዘመነ አስተርዮ ክብረ በዓላት በዳግማዊት ኢየሩሳሌም

ጥር 11/2004ዓ.ም

ዲ/ን ጌታየ መኮንን

የ2004 ዓ.ም የጌታችን የመድኀኒታችን የኢየሱስ ከርስቶስ የልደት (የገና) እና የጥምቀት በዓላት አከባበር እንደወትሮው ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን የጠበቀና ያማረ ነበር፡፡

p1180004

ካህናቱ ከታኅሣሥ 27 ቀን ጀምሮ በመድኀኒዓለም ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት መስጠት የጀመሩ ሲሆን፤ የአማኑኤል በዓል ዋዜማ ጠዋት ደወል ተደውሎ በጣም በደመቀ ሁኔታ ዋዜማው ተቆሞ ውሏል፡፡ 7 ሰዓት ሲሆን ቅዳሴ ተገባ እስከ 9 ሰዓት ቅዳሴ ተጠናቀቀ፡፡ ማታ 2 ሰዓት ማሕሌት ተደውሎ እስከ ለሊቱ 10 ሰዓት የቀጠለ ሲሆን ከ10 ሰዓት እስከ 12 ሰዓት የቅዳሴው ሥርዓት ተከናውኗል፡፡ ጠዋት 3 ሰዓት የልደት በዓል ዋዜማ ተደውሎ እስከ 10 ሰዓት እንደቦታው ትውፊትና ሥርዓት መሠረት የቦታው ቀለም እየተባለ የዋዜማው ቅኔ ለባለ ተራዎቹ እየተሰጠ ተከናውኗል፡፡ ማታ 2 ሰዓት የበዓሉ ደወል ተደውሎ ከተለያዩ የሀገራችን ክፍሎች የመጡ ምእመናን፣ የውጭ ሀገር ዜጎች፣ የቤተ ማርያምን የውስጥና የውጭ ቦታ ማሜ ጋራ የተባለውን ቦታ ከበው በእልልታ በጭብጨባ ጧፍ እያበሩ ማኅሌቱ በመዘምራኑ፣ በካህናቱ፣ በዲያቆናቱ በድምቀት ቃለ እግዚአብሔሩ እየተዘመረና እየተወረበ አድሯል፡፡

 

ከቦታው ቀለሞች   «ክርስቶስ መጽአ ውስተ ዓለም»

«ኮከብ ርኢነ ወመጽአነ ንሰግድ ሎቱ ለዘፈለጠ ብርሃነ»

 

 

ሥርዓተ ቅዳሴው እንዳለቀ የአስራ አንዱም አብያተ ክርስቲያናት ካህናትና ዲያቆናት ልብሰ ተክህኖ ለብሰው መስቀል፣ ጥላ፣ ስዕላት ይዘው ወደ ማሜ ጋራ ይወጣሉ መዘምራኑ ከሁለት ተከፍለው ከላይና ከታች ሆነው ምሳሌውም የመላእክትና የኖሎት በአንድነት እግዚአብሔርን ያመሠገኑበት ሲሆን «ቤዛ ኩሉ ዓለም ዮም ተወልደ» እያሉ እየተቀባበሉ በዓሉን በደማቅ ሁኔታ አክብረውታል፡፡ ልክ 3 ሰዓት ሲሆን ቤዛ ኩሉ አልቆ ትምሀርትና ቃለ ምዕዳን በሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብጹዕ አቡነ  ቄርሎስ ተደርጎ ልክ 4 ሰዓት የበዓሉ ፍጻሜ ሆኗል፡፡

 

በዘንድሮው ክብረ በዓል ምንም እንኳን የሀገር ውስጥ ምዕመናን ቁጥር አነስተኛ ቢሆንም፣ ከውጭ የመጡት ቱሪስቶች ቁጥር ግን ከቀድሞው የበለጠ እንደነብር ታውቋል፡፡

የጥምቀት በዓልም እንደ ልደት በዓል በቅዱስ ላሊበላ ለየት ባለ መልኩ የሚከበር በዓል ነው፡፡ ገና በዋዜማው ጠዋት 3 ሰዓት  ዋዜማ ተደውሎ እስከ 7 ሰዓት  ድረስ ዋዜማ ከተቆመ በኋላ ከ7 ሰዓት  እስከ 9 ሰዓት ድረስ ሥርዓተ ቅዳሴው ተከናውኗል፡፡

 

ልክ 10 ሰዓት ታቦታቱ ከአስራ አንዱም አብያተ ከርስቲያናት ተነስተው በቦታው ሥርዓት መሰረት ወደ 750 የሚጠጉ ካህናትና ዲያቆናት ልብሰ ተክህኖ ለብሰው መምህራኑና መዘምራኑ ጥንግ ድርብ፣ ካባ፣ ሸማ ለብሰው ጠምጥመው መቋሚያና ፀናጽል ይዘው በተራ፤ ምዕመናኑ በእልልታና በሆታ ወደ ጥምቀት ባሕሩ ተጉዘዋል፡፡

p1180055

ጥምቀት ባሕር እንደደረሱ ውዳሴ ማርያም፣ መልክዓ ማርያም፣ መልክዓ ኢየሱስና፣ መልክዓ ላሊበላ ተደግሞ ስለ ጥምቀት ትምህርት ተሰጥቶ ለውጭ ሀገር ዜጎችም በእንግሊዝኛ ቋንቋ ገለጻ ተደርጎ በጸሎት ከታረገ በኋላ ታቦታቱ ወደ መንበረ ክብራቸው ገብተዋል፡፡

 

በአጠቃላይ የጥምቀት በዓል በቅዱስ ላሊበላ ከጥንት ጀምሮ ባማረና በደመቀ ሁኔታ የሚከበር ሲሆን የውጭ ሀገር ዜጎችም በተለያዩ ጊዜያት ከዓመት ወደ ዓመት ቁጥራቸው እየጨመረ መጥቷል፡፡ በከተማው ያሉ ሆቴሎች ሁሉም ተይዘው በርካታ ቱሪስቶች ድንኳን ተከራይተው በጥምቀተ ባሕሩ ዙሪያ ማረፋቸው ታውቋል፡፡

በዚህ ዓመትም ወደ 6 የሚጠጉ የውጭ ዜጎች በጥምቀት የእግዚአብሔርን ልጅነት እንዳገኙ የቅዱስ ላሊበላ ደብር ዋና ጸሐፊ ሊቀ ሥዩማን መንግሥቴ ወርቁ ገልጸውልናል፡፡

ምሽት 2፡00 ሰዓት የበዓሉ ደወል ተደውሎ አገልግሎት የሚጀመር ሲሆን 10 ሰዓት ሲሆን ቅዳሴ ይገባል፡፡  ልክ 12፤00 ሰዓት ወደ ባሕረ ጥምቀቱ ይኬድና ጸሎቱ ይቀጥላል፡፡ 3፡00 ሰዓት ፍጻሜ ይሆናል፡፡ 5፤00 ሰዓት ሲሆን ታቦታቱ ይነሱና ወደ አብያተ ክርስቲያናቱ ይሄዳሉ፡፡ 9፡30 አካባቢም የበዓሉ ፍጻሜ ይሆናል፡፡

በዚህ ሁሉ ሂደት ልክ እንደ ቤዛ ኩሉ በዓል መዘምራኑ የክብር ልብሳቸውን ለብሰው በዝማሜ በወረብ በእልልታ በሆታ በትውፊቱና በሥርዓቱ መሠረት ይከናወናል፡፡

 

በዕለቱ ታቦታቱ ሲነሱ « ሀዲጎ ተሥዐ ወተስዐተ ነገደ» የሚለው ቃለ እግዚአብሔር ተወርቦ ይጀመርና «ወወጽአ በሰላም ቆመ ማእከለ ባሕር ገብዐ » በሚለው ወረብ ይደመደምና ታቦቱ በተለምዶ ማርያም ጥንጫ  በሚባለው ቦታ በደብሩ አለቃ ምዕዳንና ፀሎት ከተደረገ በኋላ ታቦታቱ ወደ አብያተክርስቲያናቱ ይገባሉ፡፡

ካህናቱ እንደ መላእክት ያለ ድካም በዝማሬ በዝማሜ በወረብ በአንድ ድምጽ ይዘምራሉ፡፡ የወጭ አገር ዜጎችና የሀገር ውስጥ ምእመናን ካሜራቸውን በመያዝ ቪዲዮና በፎቶ ይቀርጻሉ ያነሳሉ፡፡ እንደዚሁ ሁሉ የቃና ዘገሊላ የቅዱስ ሚካኤልና የቅዱስ ላሊበላ ታቦታት እንደቦታው ሥርዐት እንደ ጥምቀቱ ምሉዕ ካህናት አጅበውት ቃለ እግዚአብሔሩ እየደረሰ ይመለሳሉ፡፡

በከተራ የሚወርዱት 12 ታቦታት ሲሆኑ አስሩ የጥምቀት ዕለት ሲመለሱ ሁለቱ የቃና ዘገሊላ ዕለት ይመለሳሉ፡፡ አካሄዳቸውም እንደቦታው ሥርዓት ሲሆን ይህም ከጥንት የተገኘ ለመሆኑ ገድለ ላሊበላ ላይ ተገልጾ  ተቀምጦአል፡፡

ሥርዓቱ አባቶቻችን ጠበቀው በማቆየታቸው ዛሬም በዚሁ ሥርዓት ይቀጥላል፡፡ ለምሳሌ የታቦታቱ ቅደም ተከተል ይሄውም በየተራ በሰልፍ የሚሄዱበት መንገድ፣ የመዘምራን ዝማሜ፣ ጥንግ ድርብ ሻሽና ካባ ለባሽ ሆነው በሁለት ተከፍለው በተራ ይዘማሉ፡፡ ወረቡ በተራ በሊቃውንቱ እየተቃኘ ሌሎች እየተቀበሉ ይደርሳል፡፡

 

p1180070ቱሪስቶች ከዓመት ወደ ዓመት ፍሰታቸው እየጨመረ መጥቷል፡፡ ይህም ዝማሜው፣ አልባሳቱ፣ የበዓሉ ድምቀት ፣ የቦታው ሥርዓት ለየት ያለ እንዲሁም በእግዚአብሔር ድንቅ ጥበብ በቅዱስ ላሊበላ የታነጸው ህንጻ ከሊቃውንቱ፣ ሊቃውንቱ ከህንጻው ጋር አብረው የሚታዩና የማይጠገቡ በመሆናቸው እንደሆነ ሊቀ ሥዩማን ገልጸውልናል፡፡

ከሌሎች ቦታ ለየት የሚያደርገው በዓሉ የተለየ ቃለ እግዚአብሔርም አለ፡፡ ይህም በአባቶች ከቦታው ጋር እንዲስማማ ሆኖ በመደረሱ ነው፡፡

 

ለምሳሌ፡- «ዘከለሎ ብርሃን ዘከለለሎ»

«ወወጽአ በሠላም ቆመ ማዕከለ ባህር ገባዐ»

«አይኑ ዘርግብ ልብሱ ዘመብረቅ»የሚሉት ይጠቀሳሉ፡፡


በአጠቃላይ በዓሉ አመት እስኪደርስ የሚናፈቅ የሚወደድ ባላለፈ ባላለቀ ጥምቀት ለምን አንድ ጊዜ ብቻ ሆነ የሚያሰኝ ነው፡፡ ሁሉም ህብረተሰብ ወደ ቦታው ሄዶ አይቶ በረከት ቢቀበል በጣም ጥሩ ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

Begamogofa

በዲታ ወረዳ የቅዱስ ሩፋኤል ቤተ ክርስቲያን በአጽራረ ቤተ ክርስቲያን የቃጠሎ አደጋ ደረሰበት

ጥር 5/2004 ዓ.ም

ምንጭ፡- አርባ ምንጭ ማእከል

በጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከት፣ በዲታ ወረዳ፣ ጋና ደሬ ቀበሌ፣ የቅዱስ ሩፋኤል ቤተ ክርስቲያን ታኅሣሥ 29 ቀን 2004 ዓ.ም. ከሌሊቱ በስድስት ሰዓት አካባቢ በእሳት ቃጠሎ አደጋ ደረሰበት፡፡

Begamogofa

የቦታው አቀማመጥና አደጋው የደረሰበት ሰዓት ሌሊት በመሆኑ በቦታው ምንም ዓይነት ነዋያተ ቅድሳት ማትረፍ እንዳልተቻለ በቦታው የሚገኙት የደብሩ አገልጋይ ገልጸዋል፡፡ የአደጋውን መከሰት ሰምተው የመጡት የአካባቢው ምዕመናን ከሌሊት ጀምሮ ጥልቅ ሀዘናቸውን በለቅሶ ሲገልጹ እንደነበር በቦታው የተገኙት የማኅበረ ቅዱሳን አባላት ዘግበዋል፡፡

የአካባቢው ምዕመናን በወቅቱ አደጋውን ሰምተው ለመጡት ለብፁዕ አቡነ ኤልያስ የጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የቅዱሰ ሲኖዶስ አባል፣ ለሀገረ ስብከቱ የመምሪያ ሓላፊዎች፣ በአርባ ምንጭ ከተማ ለሚገኙ የደብር አለቆች፣ ለአርባ ምንጭ ማእከል የማኅበረ ቅዱሳን አባላት፣ ከመንግሥት በኩል ለጋሞ ጎፋ ዞን ፕሬዝዳንት ለአቶ ጥላሁን ከበደ፣ ለተለያዩ የመንግሥት ባለሥልጣናት፣ ለፌደራል ፖሊስ ጸጥታ አስከባሪዎች እንደተናገሩትና በተደረገው ገለፃ የአደጋው መንስኤ ታኅሣሥ 28 ቀን በወረዳው ከተማ ዛዳ በሚገኘው የአካባቢው አብያተ ክርስቲያናትም ለጥምቀተ ባሕር የሚገለገሉበትን ቦታ ላይ የፕሮቴስታንት እምነት ተከታዮች የገና በዓልን ለማክበር በመውጣታቸው ግጭት እንደነበርና ይህ በሆነ ማግስት ቤተ ክርስቲያኑ መቃጠሉን ገልጸዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ኤልያስ የጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የቅዱሰ ሲኖዶስ አባል፣ የሀገረ ስብከቱ የመምሪያ ሓላፊዎች፣ በአርባ ምንጭ ከተማ የሚገኙ የደብር አለቆች፣ የአርባ ምንጭ ማእከል የማኅበረ ቅዱሳን አባላት፣ የመንግሥት ባለሥልጣናትና የፌደራል ፖሊስ ጸጥታ አስከባሪዎች በቦታው ተገኝተው ምዕመናንን ለማረጋጋትና ለማጽናናት ችለዋል፡፡ ከዚህ በተያያዘ በወረዳው የሚገኙ አጎራባች ቀበሌዎች ውስጥ የሚኖሩ ምዕመናን ወደ ወረዳው ከተማና ቤተ ክርስቲያኑ ወደ ተቃጠለበት ቀበሌ በመድረስ ህዝቡን አጽናንተው የአብሮነት ስሜታቸውንም ሲገልጹ እንደነበር ተስተውለዋል፡፡

በዕለቱ በቃጠሎ አደጋ ለደረሰበት ቤተክርስቲያን የዕርዳታ ማሰባሰብ ሥራ የተጀመረ ሲሆን የሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት በማኅበረ ቅዱሳን የአርባ ምንጭ ማእከልና ምዕመናን በዕለቱ ማድረግ የሚችሉትን ቃል ገብተዋል፡፡ የአካባቢው ምዕመናንም ሥራውን በፍጥነት ለማስጀመር በዕለቱ እንጨት በማምጣት የተሠማሩ ሲሆን ቤተ ክርስቲያኑ በፍጥነት እንዲሠራላቸው ያላቸውን ጥልቅ ጉጉት ሲገልጹ ተስተውለዋል፡፡

Beke 1

በችግር ላይ የሚገኘው የበኬ ቅድስት ማርያም የአብነት ትምህርት ቤት እርዳታ ተደረገለት፡፡

ጥር 5/2004 ዓ.ም

በይበልጣል ሙላት
Beke 1

በአዲስ አበባ ማእከል ማኅበራዊና ልማት ክፍል የተዘጋጀ ጉዞ ወደ በኬ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን የአብነት ትምህርት ቤት የተካሔደ ሲሆን የጉዞውም ዋነኛ አላማ በአስከፊ ሁኔታ ላይ ለሚገኙት ለደብሯ የአብነት መምህራንና ተማሪዎች ጊዜያዊ የቁሳቁስ እርዳታ /ድጋፍ/ ለማድረግ እንደሆነ ተነግሯል፡፡

በጉዞውም በክፍሉ አስተባባሪነት ከምእመናንና ከማኅበሩ አባላት የተሰበሰቡና የተዘጋጁ  11 ኩንታል ስንዴ ዱቄት፣ 230 ሱሪ፣ 398 ሹራብና ቲሸርት፣ 145 ኮትና ጃኬት፣ 25 የአልጋ ልብስና አንሶላ፣ 43 የተለያዩ ልብሶች፣ 230 ግራም 249 የልብስ ሳሙና እና ለመማሪያ የሚሆኑ 11 መጻሕፍት ተበርክተዋል፡፡

በአሁኑ ሰዓት በአብነት ትምህርት ቤቱ ከ160 በላይ ተማሪዎች በ3ቱ ጉባኤያት ማለትም በቅዳሴ፣ የአቋቋም እና የቅኔ ትምህርት በመማር ላይ የሚገኙ ሲሆን ከቅርብ ጊዜBeke 3  (1) በፊት ቁጥራቸው 300 ይደርስ እንደነበር የገለጹት በመርሐ ግብሩ ላይ የተገኙት የደብሩ አስተዳዳሪ መልአከ ምሕረት አባ ገ/አማኑኤል አሮጌ አያኔ እንዲህ ቁጥራቸው ሊቀንስ የቻለው በአብነት ትምህርት ቤቱ ባለው ስር የሰደደ ችግር እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ ከቅርብ ጊዜ በፊትም ሆነ አሁን ተማሪዎቹ ሲማሩ የነበሩትና በመማር ላይ የሚገኙት የቀን ሥራ እየሠሩ ሲሆን ምንም ዓይነት የገቢ ምንጭ እንደሌላቸውና ሲያገኙ በልተው ሲያጡ ጾማቸውን እያደሩ እንደሚማሩ ገልጸዋል፡፡ በዚህም ምክንያት ጥሙን እርዛቱን መቋቋም ያልቻሉ ትምህርታቸውን እያቋረጡ የተሻለ እናገኛለን እያሉ መሔዳቸውን የደብሩ አስተዳዳሪ ገልጸው አያይዘውም በቦታው የድጓ መምህርና ተማሪዎች የነበሩ ሲሆን  ማለትም በምግብ፣ በልብስ፣ በመጠለያ ችግር ምክንያት ጉባኤው ሊበተን እንደቻለ አስታውሰዋል፡፡ ችግሩ በዚሁ ከቀጠለ አሁንም በመካሔድ ላይ ያሉት በጣም በሚያሳዝን ሁኔታ ልክ እንደ ድጓው ቁጥራቸው ቀንሶ የማይችልበት ምንም ምክንያት እንደማይኖር አስገንዝበዋል፡፡ ስለዚህ የሚመለከተው ሁሉ ከላይም ከታችም ከሊቅ እስከ ደቂቅ በጋራ ሁነን ይህ የቤተ ክርስቲያናችን ጌጥ፣ ምንጭ የሆነውን የአብነት ትምህርት ቤት በተለይም በአሁኑ ሰዓት በአስከፊ ሁኔታ ላይ ለሚገኘው ለበኬ ቅድስት ማርያም አብነት ትምህርት ቤት ልንደርስለትና ዘላቂ መፍትሔ እንዲፈለግለት በአብነት ትምህርት ቤቱ መምህራንና ተማሪዎች እንዲሁም በቤተ ክርስቲያን ስም ተማጽኖአቸውን አቅርበዋል፡፡

Beke 4ይህንንም ጥሪ ሰምቶና አጣርቶ የአዲስ አበባ ማእከል ማኅበራዊና ልማት ክፍል ከምእመኑና የማኅበሩ አባላት ጋር በመሆን ከላይ የተጠቀሰውን ጊዜያዊ ድጋፍ እንዳደረጉ የክፍሉ ተጠሪ ወ/ሪት መቅደስ አለሙ ገልጸዋል፡፡ ለወደፊትም የአብነት ትምህርቱን ችግር በዘላቂነት ለመፍታት ከምእመኑና አባላቱ እና ድጋፍ ሰጪ አካላት ጋር በመተባበር ትልቅ የጉዞ መርሐ ግብር እንደሚያዘጋጅና ቋሚ ፕሮጀክት በመቅረጽ የአብነት ትምህርት ቤቱን የመጠለያና የምግብ ችግር ለመፍታት በመንቀሳቀስ ላይ እንዳለ የገለጹት የክፍሉ ተጠሪ  አያይዘውም ምእመኑና ድጋፍ ሰጭ አካላት በዚህ የተቀደሰ አላማ እንዲሳተፉ አሳስበዋል፡፡

ከርክክቡ በኋላ ዐሳባቸውን የገለጹት አንዳንድ መምህራንና ተማሪዎች በተደረገላቸው ነገር ሁሉ መደሰታቸውን ነው፡፡

 

Beke 3  (2)የደብሩ የአቋቋም መምህር የሆኑ አባት ይህ የተደረገላቸው ድጋፍ በጣም ከመጠን በላይ እንዳስደሰታቸውና ለመግለጽ ቃላት እንደሚያጥራቸው ገልጸው ይህን ነገር እግዚአብሔር ተመልክቶ የበለጠ እንድትሠሩ ያደርጋል፤ ብለው አያይዘውም በቋሚነት ችግራቸው የሚፈታበትን መንገድ እንዲፈለግ ተማጽነዋል፡፡

 

የቅዳሴ ተማሪ የሆኑት አክሊለ ማርያም ይህ ከስጦታ ሁሉ በላይ እንደሆነና ከሁሉም በላይ ያስደሰታቸው የክርስቲያናዊ ወንድማማችነቱ የመጠያየቁ የአብሮነቱ እንዲሁም የመተሳሰቡ  ስሜት እንደሆነና ይህን ከላይ ከቤተ ክህነት ነበር የምንጠብቀው ብለው ተስፋችን ለምልሟል ልባችንም አርፏል በማለት ስሜታቸውን አጋርተዋል፡፡ አያይዘውም ለወደፊቱ በቋሚነት ልባችን ተረጋግቶ ጸንተን የምንማርበት ሁኔታ እንዲታሰብበት እና ዘላቂ መፍትሔ የሚመጣበት ሁኔታ እንዲፈጠር ተማጽነዋል፡፡

 

በአጠቃላይ የአብነት ትምህርት ቤት ችግር የቤተ ክርስቲያን ችግር የቤተ ክርስቲያን የመኖርና ያለመኖር፣ የመሠረተ እምነቷ ችግር መሆኑን አውቆ ሁሉም የዚህ የአብነት ትምህርት ቤት ችግር እንዲቀረፍ የበኩሉን አስተዋጽኦ እንዲያበረክትየአዲስ አበባ ማእከል ማኅበራዊና ልማት ክፍል አስተባባሪዋ አሳስበዋል፡፡

መካነ ጉባኤያት ወላዴ ሊቃዉንት ደብረ ሃይማኖት መካነ ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን ዕድሳት ሊደረግለት ነዉ፡፡

ታኅሣሥ 27/2004 ዓ.ም

በእንዳለ ደምስስ
  • ለዕድሳቱ 1.5 ሚሊዮን ብር ያስፈልጋል፡፡

frontመካነ ጉባኤያት የሆነዉን ታሪካዊዉንና ጥንታዊዉን ደብረ ሃይማኖት መካነ ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን ለማደስ የገቢ ማሰባሰቢያ ጉባኤ ተካሔደ፡፡ታኅሣሥ 22 ቀን 2004 ዓ.ም . በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ሁለገብ አዳራሽ በተካሄደዉ በዚህ ጉባኤ የአራቱ ጉባኤያት የትርጓሜ መምህር የሆኑት ሊቀ ሊቃዉንት ዕዝራ ሐዲስና የደብረ ሃይማኖት መካነ ኢየሱስ አስተዳዳሪና የድጓ መምህር የሆኑት መልአከ ሃይማኖት ሲሳይ አሰፋ ጉባኤያቸዉን ትተዉ የተገኙበት ሲሆን፣ ከአዲስ አበባም በአሁኑ ጊዜ የሊቃዉንት ጉባኤ ሰብሳቢ የሆኑት መልአከ ሰላም ዐምደ ብርሃን እና  መልአከ ታቦር ተሾመ ዘሪሁን፣ ሊቀ ስዩማን ራደ አስረስና ሌሎች የሊቃዉንት ጉባኤ አባላት እንዲሁ ም በሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳዉሎስ ከፍተኛ መንፈሳዊ ትምህርት ቤት የሐዲስ ኪዳን ትርጓሜ መምህር የሆኑትን መጋቤ ሐዲስ ስቡሕ አዳምጤን ጨምሮ በቦታዉ የተማሩና የጉባኤ ቤቱን ታሪክ የሚያዉቁ በርካታ ሊቃዉንት በጉባኤዉ ላይ ተገኝተዋል፡፡

 

 

በጉባኤዉ ላይ ዲያቆን ያረጋል አበጋዝና ሊቀ ሊቃዉን ዕዝራ ሐዲስ ትምህርተ ወንጌል ሰጥተዋል፡፡የቦታዉ የድጓ መምህርና የቤተ ክርስቲያኑ አgubae z mekane Eyesus 047ስተዳዳሪ መልአከ ሃይማኖት ሲሳይ አሰፋ አጂግ በሚመስጠዉ ድምጻቸዉ ያሬዳዊ ወረቦችን ሲያንቆረቆሩ ሊቃዉንቱን ሁሉ አስደምመዋል፡፡

የቀዳሜ ዜማ ሊቃዉንት ማኅበር አባላት የሆኑት ሊቃዉንተ ቤተ ክርስቲያን፣ የታዕካ ነገሥት በዓታ ለማርያም ገዳም ሰንበት ትምህርት ቤትgubae z mekane Eyesus 118 መዘምራን ልምላሜ ነፍስ የሚያስገኙ ወረቦችን አቅርበዋል፡፡ የደብረ ኃይል ቅዱስ ራጉኤል ጎልማሶች ጉባኤ መዘምራንና ዲያቆን ምንዳዬ ብርሃኑም ሕዝቡን ያሳተፉ ጥዑም ዝማሬዎችን አሰምተዋል፡፡ ጉባኤዉ ከላይ ከተገለጹት መርሐ ግብራት በተጨማሪ የቦታዉን መልክአ ምድራዊ አቀማመጥ፣ ቤተ ክርስቲያኑን፣ አብያተ ጉባኤያቱንና የክብረ በዓል ሥርዓቱን የሚያሳይ 10 ደቂቃ ቪዲዮ ከቀረበ በኋላ  በሊቀ ስዩማን ራደ አስረስና በመልአከ ታቦር ተሾመ ዘሪሁን ከቦታዉ ተምረዉ ለታላቅ መዓርግ ስለበቁት ሊቃዉንትና ስለ ጉባኤቤቱና ስለ ቤተ ክርስቲያኑ ታሪክ ሰፊ ገለጻ ቀርቧል፡፡

 

በዐጼ አድያም ሰገድ ኢያሱ ዘመነ መንግሥት የተተከለዉ ጥንታዊዉና ታሪካዊዉ ደብረ ሃማኖት መካነ ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን በሦስት ታላላቅ ጉባኤያቱ የታወቀ ነበር፡፡በቅዱሳት መጻሕፍት ትርጓሜ ቤተ ጉባኤ፣ በቅኔ ቤተ ጉባኤ እና በድጓ ቤተ ጉባኤ፡፡በሦስቱም አብያተ ጉባኤያት ታላላቅ ሊቃዉንትን ለሀገሪቱም ሆነ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ሲያበረክት የቆየዉ ይህ ታሪካዊ ቦታ እስከ 1950ዎቹ ሦስቱም ጉባኤያት የነበሩት ቢሆንም በአሁኑ ጊዜ ግን የቅኔ ጉባኤ ቤቱ ታጥፎ የትርጓሜ መጻሕፍቱና የድጓ ጉባኤዎቹ ግን አሁንም ሳይታጎሉ የሚሰጥበት ቦታ ነዉ፡፡

ቤተ ክርስቲያኑ በንግሥተ ንግሥታት ዘዉዲቱ ዘመን በጥሩ ሁኔታ በዘመናዊ መንገድ ተሠርቶ ከተጠናቀቀ በኋላ ወዲያዉኑ ጠላት (ጣልያን) ወደ ሀገራችን በመግባቱ ምክንያት ቤተ ክርስቲያኑ ተቃጥሎ ነበር፡፡ በጊዜዉ በአካባቢዉ ከነበሩት ስዉራን አበዉ አንዱ በግንቦት ወር መጀመሪያ ላይ ተገልጠዉ በ 7 እሳት ይወgubae z mekane Eyesus 018ርዳል እያሉ ትንቢት ሲናገሩ የሰሙት አበዉ ታቦታቱን መጻሓፍቱንና ንዋያተ ቅድሳቱን በሙሉ ይዘዉ በአቅራቢያዉ ወደምትገኘዉ ዋሻ ማርያም የምትባል የዋሻ ዉስጥ ቤተ ክርስቲያን አስገቡት፡፡ እንደ ተነገረዉም በተጠቀሰዉ ቀን ጣሊያን አካባቢዉንና ቤተ ክርስቲያኑን ሲያቃጥል የተጠቀሱት ንብረቶች በሙሉ ከዉድመት ዳኑ፡፡ ጣልያን ድል ተነሥቶ ከሀገር እስኪወጣ ድረስም ለሦስተ ዐመታት ያህል በዚያ ዋሻ ዉስጥ ተቀምጦ ሊቃዉንቱና ማኅበሩም በየዐመቱ የልደትን በዓል በዚያ ዋሻ ዉስጥ በሐዘን ሲያከብሩ አሳልፈዋል፡፡ እንደ ሊቀ ስዩማን ራደ አስረስ ገለጻ የመልክአ ኢየሱስ ነግሦች ከሆኑት (ከሚወረቡት) የመጨረሻ የሆነዉ ከምዕራጉ ‹‹ኢየሱስ ክርስቶስ ሊቀ ካህናቲነ፣ አስተጋብአነ ኀበ ትረፍቅ መካነ፤ እስመ ዝርዋን አግብርቲከ ንህነ›› በለቅሶና በሐዘን ይወረብ ነበርና ሐዘኑና ሱባኤዉ ጠላት ጣሊያንን ለመመለስ ጠቅሟል፡፡ ጣሊያን ከሀገራችን ከወጣ በኋላ በመቃረቢያ ታቦቱ ገብቶ መምህራኑም ጉባኤያቸዉን ተክለዉ ጥቂት ዐመታት እንደቆየ በቦታዉ ላይ የትርጓሜ መምህር በነበሩትና ከጠላት መመለስ በኋላ ከመጀመሪያዎቹ ጳጳሳት አንዱ በነበሩት የጥንቱ አቡነ ሚካኤል ( የቅዳሴ ትርጓሜን አዘጋጅተዉ ያሳተሙት) አሳሳቢነትና አስተባባሪነትም ጭምር በንጉሡ በዐፄ ኃይለ ሥላሴ ፈቃድ እንደገና አሁን በሚታየዉ መልኩ ተሠርቶ በእግዚአብሔር ቸርነት ተጠናቀቀ፡፡

ይህ አሁን ያለዉ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ግንባታዉ ከተጀመረ ከአንድ ዐመት በኋላ ራሳቸዉ ንጉሠ ነገሥቱ እቦታዉ ድረስ ሄደዉ ግንባታዉንም በቦታዉ ተቀምጠዉ በማሰራት ላይ የነበሩትን ብጹዕ አቡነ ሚካኤልንም አይተዉ ተመልሰዋል፡፡በጊዜዉ በቦታዉ ላይ ቅኔዉንና ትርጓሜ መጻሕፍቱን አንድ ላይ አድርገዉ ያስተምሩ የነበሩት እጅግ ስመ ጥር የነበሩት የኔታ  ገብረ ጊዮርጊስ ነበር፡፡ በዚህ ወቅት በድጓ ቤት ያሉትን ሳይጨምር ከ450 በላይ የቅኔና የትርጓሜ መጻሕፍት ተማሪዎች የነበሩበት ጊዜ ነበር፡፡

ይህ አሁን ያለዉ ቤተ ክርስቲያን ተፈጽሞ በሚመረቅበት ጊዜ ደግሞ ንጉሠ ነገሥቱ ተጠብቀዉ ባይገኙም የጎንደሩ ገዥ ደጃዝማች ክፍሌ ዳዲ እና   የዚያን ጊዜዉ ጳጳስ የኋላዉ ፓትርያርክ አቡነ ቴዎፍሎስና ታላቁ አቡነ ዮሐንስ ከሌሎች የጊዜዉ የመንግሥት ባለ ሥልጣናትና ሊቃዉንተ ቤተ ክርስቲያን ጋር ተገኝተዉ እንደነበርም ተገልጾአል፡፡

Beataደብረ ሃይማኖት መካነ ኢየሱስ የሃይማኖት አባቶችን ለሀገሪቱ ከማበርከቱም በላይ በኢትዮጵያ ካቶሊኮች ገብተዉ ከወጡበት የጥንቱ ጊዜ በኋላ መልኩን ቀይሮ የቤተ ክርስቲያን ሊቃዉንትን ሲያበጣብጥ የቆየዉ የቅባትና የጸጋ ሰርጎ ገብ ፈጽሞ ካልረገጣቸዉ የሰሜን ኢትዮጵያ የትርጓሜ ትምህርት ቤቶች አንዱ መሆኑ በሊቃዉንቱ በተደጋጋሚ ተመስክሮለታል፡፡የደብሩ አስተዳዳሪና የድጓ መምህር መልአከ ሃይማኖት ሲሳይ አሰፋ በታሪክ የሚታወሱትን ሊቃዉንት ሲያወሱ የታች ቤት ትርጓሜ መሥራች የሚባሉት መምህር ኤስድሮስ የዚህ ቦታ መምህር እንደ ነበሩና ጣና ገብተዉ መጻሕፍትን መርምረዉ የታች ቤቱን ትርጓሜ ጎንደር ልደታ ላይ ከማስተማራቸዉ በፊት መካነ ኢየሱስ ላይ ተምረዉ ከዚያም ወንበሩን ተረክበዉ ማስተማራቸዉንና በኋላም መጥተዉ በቦታዉ ጥቂት ጊዜያትን ከቆዩ በኋላ እዚያዉ አርፈዉ መቀበራቸዉን አስረድተዋል፡፡ የቦታዉን ታላቅነት አስመልክቶ በሊቃዉንቱ ዘንድ ብዙ የሚነገርለት መሆኑን ያወሱት መልአከ ታቦር ተሾመ ዘሪሁንም በታላቁ ሊቅ የኔታ ገብረ ጊዮርጊስ ከተቀኙት መወድስ ዉስጥ ፤

‹‹… ቤተ ጽድቅሂ ቤተ ሥላሴ መካነ ኢየሱስ ዉእቱ፣
እስመ ኢያንቀለቅል ለዓለም ሃይማኖት መሠረቱ፣
ባሕቱ ድልዉ መልዕልተ ሰማያት ሰባቱ፣
መካነ ኢየሱስ መንበረ አብ ዘይጸዉርዎ አርባዕቱ፡፡…››

የሚለዉን ዘርዕ በማሰማት በምሥጢር ‹ ልክ እንደ አርባእቱ እንስሳ ኪሩቤል አራቱ ጉባኤያተ መጻሕፍትን በመዘርጋትና የማይናወጽ የሃይማኖት መሠረት በመሆን ኑፋቄንም ባለማስደረስ  መካነ ኢየሱስ በእዉነት የሥላሴ ቤት የእግዚአብሔር መንበሩ ነዉ › ተብሎ ይነገርለት እንደነበር አስረድተዋል፡፡ መልአከ ሰላም ዐምደ ብርሃንም የኔታ ገብረ ጊዮርጊስን ከመካነ ኢየሱስ ወደ አክሱም እንዲሄዱ ለአክሱሞች ከፍተኛ ዋስትና የሰጠዉ ይሄዉ በሃይማኖት ነቅዕ ጥርጣሬ የሌለዉ ጉባዔ የሚሰጥበት መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ቦታዉ ለቅርቧ ኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንም ያበረከታቸዉ ሊቃዉንት እጅግ ብዙዎች ናቸዉ፡፡እንደ ሊቀ ስዩማን ራደ አስረስ ገላጻ በ1921 ዓ ም ግብጽ ወርደዉ ከተሾሙት ከዐራቱ አንዱ የሆኑት ጎሬ ላይ በጣልያን እንደ አቡነ ጴጥሮስ ሰማዕትነት የተቀበሉት ብጹዕ አቡነ ሚካኤል በዚህ ቦታ በትምህርት ካለፉት ዉስጥ አንዱ ናቸዉ፡፡ በኋላም በጣልያን ሁለቱ አበዉ ማረፋቸዉን በማየት የኢትዮያ ሊቃዉንት ከሾሟቸዉ ዉስጥ አቡነ ዮሐንስ የተባሉት ሐዲስ ተክሌ የተማሩት ደብረ ሃይማኖት መካነ ኢየሱስ ነበር፡፡ ከጣልያን መመለስ በኋላም በ1941 ከተሾሙት ከቀዳሚዎቹ ሊቃነ ጳጳሳት አንዱ ከሆኑት ከብጹዕ አቡነ ሚካኤል ጀምሮ እነ አቡነ በርተሎሜዎስ፣ አቡነ ኤልያስ (አሁን ስዊድን ያሉት) የኋላዉ አቡነ ኤልያስ (የቀለም ቀንዱ ሊቀ ጉባኤ አስበ)፣ ተጠቃሾች ሲሆኑ ከሊቃዉንቱም እነ ርዕሰ ደብር ጥዑመ ልሣን፣ መልአከ ታቦር ተሾመ ዘሪሁን፣ ሊቀ ሥዩማን ራደ አስረስ፣ መልአከ ሰላም መርዓዊ ተበጀ፣ … ተቆጥረዉ የማያልቁ የብሉይ፣ የሐዲስ፣የመጻሕፍተ ሊቃዉንት፣ የመጻሕፍተ መነኮሳት፣ የቅኔና የዜማ ሊቃዉንትን አፍርቷል፡፡

ቤተ ክርስቲያኑ ባለፉት ሃምሳ ዐመታት ዉስጥም በቦታዉ ብሉይና ሐዲስን በማስተማር፣ የተጣሉትን ከማስታረቅ ጋር በብሕትዉና በመኖር የgubae z mekane Eyesus 130ሚታወቁት መጋቤ ሐዲስ ኃይለ ሚካኤል ብዙ ደቀ መዛሙርትን በማፍራት ያገለገሉበት ሲሆን እርሳቸዉ በዕርጅና ማስተማሩን ሲያቆሙ በአሁኑ ጊዜ ደግሞ ሐዲሳቱን ከእርሳቸዉ ብሉያቱን ደግሞ ጎንደር ዐቢየ እግዚእ ከየኔታ ፀሐይ የተማሩት የኔታ ሐረገወይን ተተክተዉ በማስተማር ላይ ይገኛሉ፡፡ የደብሩ አስተዳዳሪ የሆኑት መልአከ ሃይማኖት ሲሳይ አሰፋም በቦታዉ ላይ ድጓዉን በማስተማርና ብዙ መምህራንና ደቀ መዛሙርትን በማፍራት ከሃያ አምስት ዐመት በላይ ኖረዉበታል፡፡

ቦታዉ ብዙ ታሪካዊ ቅርሶችን የያዘ ከመሆኑም በላይ ከጥንት ጀምሮ እጅግ ብዙ ሕመምተኞች (ብዙ የእስልምና ተከታዮችን ጨምሮ) የሚፈወሱባት የኪዳነ ምሕረት ጸበል ይገኝበታል፡፡

በአሁኑ ጊዜ ቆርቆሮዉ አርጅቶ በማፍሰስ ላይ ከመሆኑም በላይ ሌሎቹንም ጨምሮ ከ 1.5 ሚሊዮን ብር በላይ ወጭ የሚጠይቅ እድሳት እንደሚያስፈልገዉ በባለሞያዎች የተጠናዉ ጥናት ያመለክታል፡፡ እንደ ባለሞያዎቹ ገለጻ 750 ቆርቆሮና ለጣራ ሥራዉ የሚሆኑ የተለያዩ ጣዉላዎች፣በጣዉላ የሚሰራ ኮርኒስ፣ የኤሌክትሪክ፣የፍሳሽ፤ 24 ቆመ ብእሲዎች ወይም አምዶች (Columns)፣ የግቢዉን በርና ሌሎቹንም ያካትታል፡፡ ቤተ ክርስቲያኑ የሚገኘዉ ገጠር ዉስጥ ከመሆኑ ጋር ተያይዞ የሌሎቻችንን በተለይም በቦታዉ ላይ በመማርና ከተማሩት አገልግሎት በማግኘት ላይ ያሉትን እንዲሁም ለኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን አሁንም ድረስ ከፍተኛ አስተዋጽኦ በማድረግ ላይ የሚገኘዉን ታሪካዊዉን ቦታ በመርዳት እንደ ቀድሞዉ ሁሉ ለኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ያለዉን አስተዋጥኦ ማሳደግ እንደሚጠበቅ በዕለቱ ከነበሩት በመልአከ ታቦር ተሾመ ዘሪሁንና በሊቃዉንት ጉባኤ ሰብሳቢዉ መልአከ ሰላም ዐምደ ብርሃን በአጽንዖት ተገልጾአል፡፡

በመርሐ ግብሩ ተሳታፊዎች ጥያቄ መሠረት ሥራዉን ለመርዳት ለሚፈልጉ በስልክ ቁጥሮች
0911 68 93 22
0911 10 95 84
0911 13 73 50

በመደወልና በማነጋገር በዐይነትም ሆነ በገንዘብ መርዳትና ለለገሱት እርዳታም ሕጋዊ ደረሰኝና በዐይነትም ከሆነ የተላከዉ ዕቃ መድረሱን ማረጋገጫ ባለ ማኅተም ደብዳቤ መቀብል እንደሚገባ ተገልጾ ጉባኤዉ በጸሎት ተጠናቅቋል፡፡ በዚህ አጋጣሚ ከቀኑ 8፡30 ጀምሮ እስከ 12፡ 30 ድረስ በቆየዉ በዚህ ረጂም ጉባኤ ተሳታፊዎቹ በትዕግስት ጸንተዉ የሊቃዉንቱን ትምህርቶችና ገለጻዎች እነዲሁም ወረቦችና ዝማሬዎች ሲኮመኩሙ እንዲዉሉ ያስቻለዉ ጉባኤዉ የገቢ ማሰባሰቢያ ሳይሆን የትምህርትና የዝማሬ ብቻ መስሎ በመዘጋጀቱ እያመሰገንን ሌሎቹም አራአያዉን ሊከተሉት የሚገባ መሆኑን ሳንጠቁም አናልፍም፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!!
30

እረኝነት እንደ አፍርሃት ሶርያዊ አስተምህሮ

ታኅሣሥ 24/2004 ዓ.ም

ትርጉም

በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ

መግቢያ

አፍርሃት ያዕቆብ ዘንጽቢን እና “የፋርሱ ጠቢብ” በሚሉ ስያሜዎቹ የሚታወቅ አባት ሲሆን በዐራተኛው ክፍለ ዘመን መግቢያ ላይ የተነሣ ሶርያዊ ተጠቃሽ  ጸሐፊ ነው፡፡ በእርሱ ዘመን ማኅልየ ማኅልይ ዘሶርያና የቶማስ ሥራ የሚባሉት ሥራዎች እንደሚታወቁ ይታመናል፡፡ ስለአፍራሃት የሕይወት ታሪክ ብዙ የሚታወቅ ነገር ባይኖርም አንዳንድ ጥንታዊ ታሪክ ጸሐፊያን አፍራሃት በአሁኑዋ ኢራቅ ትገኝ በነበረችው ማር ማታያ ተብላ በምትታወቀው ገዳም ሊቀ ጳጳስ እንደነበረ ጽፈው ይገኛሉ፡፡ ይህ ግን ተቀባይነት የለው፡፡ አፍራሃት ሃያ ሦስት ድርሳናትን የጻፈ ሲሆን እነርሱም የተለያዩ ርእሶች ያሉዋቸው ናቸው፡፡ እርሱ ከጻፈባቸው ድርሰቶች መካከል ስለእምነት ፣ ስለፍቅር፣ ስለጾም ፣ ስለጸሎት፣ በዘመኑ ስለነበረው የቃልኪዳን ልጆችና ልጃገረዶች፣ ስለትሕትና ጽፎአል፡፡ አፍርሃት ከቅዱስ ኤፍሬም ጋር ለሶርያ ሥነ ጽሑፍ ፋና ወጊ የሆነ ጸሐፊ ነው፡፡  እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ በእረኝነት ላይ የፃፈውን እንመለከታለን፡፡

እረኞች የሕይወት ምግብን ይሰጡ ዘንድ በመንጋው ላይ የተሾሙ አለቆች ናቸው፡፡ መንጋውን የሚጠብቅና ስለእነርሱ የሚደክም እረኛ እርሱ መንጋውን ለሚያፈቅረውና ራሱን ስለመንጎቹ ለሰጠው መልካም እረኛ እውነተኛ ደቀመዝሙር ነው፡፡ ነገር ግን መንጋውን ከጥፋት የማይመልስ እርሱ ለመንጋው ግድ የሌለው ምንደኛ ነው፡፡

እናንተ እረኞች ሆይ በጥንት ጊዜ የነበሩትን ቅዱሳን እረኞችን ምሰሉአቸው፡፡ ያዕቆብ የላባን በጎች ያሰማራ፣ በትጋትና በድካም ይጠብቅ30 ነበር፡፡ በዚህም ከአምላኩ ዘንድ ዋጋ አግኝቶበታል፡፡ አንድ ወቅት ያዕቆብ ለላባ  “ሃያ ዓመት ሙሉ ከአንተ ጋር ነበርሁ በጎችህና ፍየሎችህ አልጨነገፉም የመንጎችህንም ጠቦቶች አልበላሁም አውሬ የሰበረውን አላመጣሁልህም ነበር፤ እኔ ስለ እርሱ እከፍልህ ነበርሁ፤ በቀንም በሌሊትም የተሰረቀውን ከእጄ ትሻው ነበር፡፡ የቀን ሀሩር የሌሊት ቁር ይበላኝ ነበር ፤ እንቅልፍ ከዐይኔ ጠፋ”(ዘፍ.፴፩፥፴፰-፴፱)ብሎት ነበር፡፡  እናንተ እረኞች ይህን እረኛ ለመንጎቹ ምን ያህል እንዲጠነቀቅ  አስተዋላችሁን? በሌሊት እንኳ እነርሱን ለመጠበቅ በትጋት ያለእንቅልፍ የሚተጋ እነርሱንም ለመመገብ በቀን  የሚደክም  እውነተኛ እረኛ ነበር፡፡

ዮሴፍና የእርሱ ወንድሞች ሁሉ እረኞች ነበሩ፤ ሙሴ የበጎች እረኛ ነበር፤ ዳዊትም እንዲሁ እረኛ ነበር፡፡ አሞጽም ላሞችን ያግድ ነበር፡፡ እነዚህ ሁሉ መንጎቻቸውን በመለመለመ መስክ ማሰማራት የሚያውቁ እረኞች ናቸው፡፡ ወዳጄ ሆይ  እግዚአብሔር እነዚህን እረኞች አስቀድመው በጎችን በኋላም ሰዎችን እንዲጠብቁ ስለምን እንዳደረጋቸው ተረዳህን? መልሱ ግልጽ ነው፤ መንጎቻቸውን እንዴት መጠበቅና ስለእነርሱ ሲሉ ምን ያህል መድከም እንዳለባቸው ሊያስተምራቸው በመፈልጉ ነበር፡፡ ይህንን የእረኝነት ሓላፊነት ከተማሩ በኋላ ለእረኝነት ተቀቡ፡፡ ያዕቆብ የላባን በጎች በብዙ ድካምና ትጋት ጠበቀ፤ በለመለመ መስክም አሰማራ፡፡ ከዛም ልጆቹን በአግባቡ ወደ መምራት ተመለሰ፣ የእረኝነት ሙያንም ለልጆቹ አስተማረ፡፡ ዮሴፍ በጎችን ከወንድሞቹ ጋር በመሆን  ይጠብቅ ነበር፡፡ ስለዚህም በግብጽ እጅግ ብዙ ሕዝብን ይመራና ልክ እንደ መልካም እረኛ ያሰማራ ዘንድ ተሾመ፡፡ ሙሴ የአማቱን በጎች ይጠብቅ ነበር፡፡

 

በመቀጠል ወገኖቹን ይመራ ዘንድ ተመረጠ፡፡ እርሱም እንደ መልካም እረኛ ሕዝቡን በለመለመ መስክ አሰማራ፡፡ ሕዝቡ የጥጃ ምስልን ሠርቶ እግዚአብሔር አምላክን በማሳዘናቸው ምክንያት ሊያጠፋቸው ቆርጦ ሳለ ሙሴ ስለሕዝቦቹ ተገብቶ እግዚአብሔር አምላክ ይቅር እንዲላቸው ዘንድ “አሁን ይህን ኃጢአታቸውን ይቅር በላቸው፤ ያለዚያ ግን ከጻፍከው መጽሐፍህ እባክህ እኔን ደምስሰኝ” (ዘጸአ.፴፪፥፴፪) ብሎ ጸለየ፣ እግዚአብሔር አምላኩን ተለማመነው፡፡ በመንጎቹ ፈንታ ነፍሱን የሚሰጥ እርሱ እጅግ መልካም እረኛ ነው፡፡ ስለሚመራው ሕዝብ ነፍሱን የሚሰጥ እርሱ ትክከለኛ መሪ ነው፡፡ እርሱ ስለመንጎቹ ደጀን ሆኖ የሚጠብቅና የሚመግብ ርኅሩኅ አባት ሊስኝ የሚገባው፡፡ መንጋውን እንዴት ማሰማራት እንደሚችል የሚያውቀው አስተዋዩ እረኛ ሙሴ እጁን ጭኖ መንፈሱን ላሳደረበት ለመንፈስ ልጁ ለኢያሱ ወለደ ነዌ፣ የእግዚአብሔርን መንጋ እንዲያሰማራ የእስራኤልንም ሠራዊት እንዲመራ የእረኝትን ሙያ አስተምሮት ነበር፡፡ እርሱ ጠላቶቹን ሁሉ ድል በመንሳትና ሀገራቸውንም በመውረስ፣ የመሰማሪያ መስክ በመስጠትና ምድሪቱንም ያርፉባትና ለበጎቻቸውም ማሰማሪያ ያገኙ ዘንድ አድርጎ አካፈላቸው፡፡

 

እንዲሁ ንጉሥ ዳዊት የአባቱን በጎች ይጠብቅ ነበር፡፡ ከዚህም ነው ሕዝቡን ይመራ ዘንድ የተቀባው፡፡ እርሱ ከልቡ ሕዝቡን ወደ አንድነት መራ፤ በእጁም ጥበብ መንጋውን አሰማራ፡፡ ዳዊት መንጎቹን ወደ መቁጠር በመጣ ጊዜ በእነርሱ ላይ የእግዚአብሔር ቁጣ ነደደ፤ ሕዝቡም እግዘአብሔር ባመጣው ቸነፈር ምክንያት ማለቅ ጀመረ፡፡ ዳዊት ግን በመንጎቹ ምትክ እርሱና ቤቱ ላይ ቅጣቱ እንዲፈጸም ጠየቀ፡፡ በጸሎቱ ስለእነርሱም “ጌታ ሆይ እኔ በድያለሁ፤ ጠማማም ሥራ አድርጌአለሁ፤ እነዚህ በጎች ግን እነርሱ ምን አደረጉ፤ እጅህ በእኔና በአባቴ ቤት ላይ አንድትሆን እለምንሃለሁ፡፡”(፪ሳሙ.፳፬፥፲፯)ብሎ እግዚአብሔር አምላክን አጥብቆ ተማጸነ፡፡ ነገር ግን ስለመንጎቻቸው ግድ ስለሌላቸው እረኞች፣ ለእነዚያ እራሳቸውን ብቻ ስለሚያሰማሩ እረኞች ነቢዩ እንዲህ ይወቅሳቸዋል “መንጎቼን የምታጠፉና የምትበትኑ እናንተ እረኞች ሆይ የጌታን ቃል ስሙ እግዚአብሔር እንዲህ ብሎአል፡፡ እረኛ መንጎቹን እንዲጎበኝ አንዲሁ እረኞችን የምጎበኝበት ጊዜ ይመጣልና ወዮላችሁ፡፡  በዚያን ጊዜ በጎቼን ከእጃችሁ እፈልጋቸዋለሁ፡፡

 

እናንተ ሰነፍ እረኞች ሆይ ከበጎቼ ፀጉር ለበሳችሁ፡፡ ከሰባውም ተመገባችሁ በጎቼን ግን አላሰማራችሁም፣ የታመመውን አላዳናችሁም፣ የተሰበረውን አልጠገናችሁም፣ የደከመውን አላበረታችሁም የጠፋውንና የባዘነውን አልፈለጋችሁም፣ ብርቱውንና የሰባውን አሰማራችሁ ነገር ግን እነርሱን በግፍ አጠፋችኋቸው፡፡ እናንተ የሰባውን ገፋችሁ በላችሁ፣ ከእግራችሁ ሥር ያለውን ረገጣችሁ፡፡ እናንተ ከጥሩ ውኃ ትጠጣላችሁ ከእናንተ የተረፈውን ውኃ ግን በእግራችሁ ታደፈርሳላችሁ፡፡ የእኔ በጎች እናንተ ባጠፋችሁት መስክ ታሰማሯቸዋላችሁ፡፡ በእግራችሁም ያደፈረሳችሁትንም ውኃ ታጠጧቸኋላችሁ” ይላል፡፡ (ዘካ. ፲፩፥፲፭-፲፯)  እነዚህ እረኞች ስስት የሠለጠነባቸው፣ የማያስተውሉ እረኞች እና ባለሙያተኞች ናቸው፡፡ እነዚህ መንጎቻቸውን አይመግቡም ወይም አይጠብቁም ወይም ለተኩሎች አሳልፈው የሚሰጡ ጨካኝ እረኞች ናችው፡፡ ነገር ግን የእረኞች አለቃ ይመጣል፤ መንጎቹንም በየስማቸው ይጠራል፤ ይጎበኛቸዋል፤ ስለመንጎቹም ደኅንነት ይመረምራል፡፡ የበጎቹንም እረኞች ከፊቱ ያቆማቸዋል፤ እንደ በደላቸውም መጠን ይከፍላቸዋል፤ እንደሥራቸውም መጠን ይመልስባቸዋል፡፡

መንጎቻቸውን በመልካም ላሰማሩ እረኞች ግን የእረኞች አለቃ ደስ ያሰኛቸዋል፤ ዘለዓለማዊ ሕይወትንና ዕረፍትን ይሰጣቸዋል፡፡ አንተ የማታስተውል ሰነፍ እረኛ ሆይ ሰለመተላለፍህ ቀኝ ክንድህንና ቀኝ ዐይንህን ታጠፋታለህ፡፡ ምክንያቱም ስለበጎቼ የሚሞተው ይሙት፤ የሚጠፋውም ይጥፋ ቅሬታም ካለው ሥጋውን እቀራመተዋለሁ የምትል ሆነሃልና፡፡ ስለዚህም ቀኝ ዐይንህን አጠፋዋለሁ ቀኝ እጅህንም ልምሾ አደርገዋለሁ፡፡ መማለጃን የሚጠብቁትን ዐይኖችህ ይጠፋሉ፤ በጽድቅ የማይፍርደውም እጆችህም የማይጠቅሙ ልሙሾዎች ይሆናሉ፡፡  ብታስተውለው እንደ አንተ በመስኩ ላይ የተሰማሩት በጎቼ የሰዎች ልጆች ናቸው፡፡ እኔ ግን ያንተ ጌታ የሆነኩ አምላክህ ነኝ፡፡ እነሆ በዛ ጊዜ መንጎቼን በለመለመ መስክ በመልካም አሰማራቸዋለሁ፡፡ “መልካም እረኞ ነፍሱን ስለበጎቼ አሳልፎ ይሰጣል፡፡” እንዲሁም “ወደዚህ የማመጣቸው ሌሎች በጎች አሉኝ፡፡ እናም አንድ መንጋ ይሆናሉ፡፡” አንድም እረኛ ይኖራቸዋል፡፡ አባቴ ስለሚያፈቅረኝ ስለበጎቼ ራሴን አሳልፌ እሰጣለሁ፡፡” እንዲሁም “እኔ በር ነኝ ሁሉም በእኔ በርነት ይገባል በእኔም ምክንያት በሕይወት ይኖራል ፡፡ እናም ይወጣል ይገባል ይወጣል ይላል ጌታ፡፡…”

Picture3

ማኅበረ ቅዱሳን ሐዋርያዊ አገልግሎት በአርሲ ሀገረ ስብከት አካሔደ

ታኅሣሥ 20/2004 ዓ.ም

በእንዳለ ደምስስ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን ሐዋርየዊ Picture3አገልግሎት በአርሲ ሀገረ ስብከት ከኅዳር 29/2004 ዓ.ም እስከ ታኅሣሥ 10/2004 ዓ.ም ለ11 ተከታታይ ቀናት በተለየዩ ወረዳዎች አካሔደ፡፡ 27 አባላት የተሳተፉበት ሐዋርያዊ አገልግሎት በተመረጡ 6 ወረዳዎች ውስጥ በሚገኙ ቤተ ክርስቲያናት እንዲሁም በአሰላ ከተማ በተሳካ ሁኔታ የተከናወነ ሲሆን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ያፈራቻቸው የማኅበረ ቅዱሳን ሰባኪያነ ወንጌል አማካይነት በአውደ ምሕረት ላይ ለምእመናን ሰፋ ያለ የወንጌል ትምህርት ተሰጥቷል፡፡ በማኅበሩ መዝሙር ክፍል አባላት አማካይነት ከአባቶች እግር ስር ቁጭ ብለው የተማሩትን የቤተ ክርስቲያኗን ሥርዓትና ትውፊት የጠበቀ ያሬዳዊ ዝማሬ አቅርበዋል፡፡

በአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በብፁዕ አባታችን አቡነ ናትናኤል መልካም ፈቃድ ማኅበረ ቅዱሳን በያዘው እቅድ መሠረት የሐዋርያዊ የወንጌል አገልግሎት እንዲካሔድ በመፍቀድና በመከታተል እንዲሁም አባታዊ ምክራቸውንና ቡራኬ በመለገስ፤ በጸሎት በማገዝ አገልግሎቱ የተሳካ እንዲሆን አባታዊ ድርሻቸውን ተወጥተዋል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን በ6ቱ ወረዳዎች ማለትም በአሳሳ ደብረ ሰላም ቅዱስ ገብርኤል፤ በሳጉሬ ደብረ ገነት ልደታ ለማርያም፣ በበቆጂ ደብረ ፀሐይ ቅዱስ ጊዮርጊስ፤ በኢተያ ቅዱስ በዓለወልድ፤ በሁሩታ ደብረ መዊዕ ቅድስት ድንግል ማርያም፣ በአሰላ ደብረ መድኃኒት መድኀኔዓለም እና በዴራ ደብረ መድኀኒት መድኀኔዓለም ቤተ ክርስቲያናት በእያንዳንዳቸው ለ2 ቀናት /በበቆጂ አንድ ቀን ብቻ/ የቆየ የወንጌል ትምህርትና ያሬዳዊ ዝማሬ ቀርቧል፡፡ አገልግሎቱም ምዕመናን በሃይማኖታቸው ጸንተው እንዲቆሙ ከተለያዩ ኢ አማኒያን የኑፋቄ ትምህርት እንዲጠበቁ፤ ከእነሱም ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የምትሻውን አገልግሎት እንዲያበረክቱ ፤ንስሐ ገብተው የጌታችን የመድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ተቀብለው የመንግሥቱ ወራሾች ይሆኑ ዘንድ መሠረታዊ የቤተ ክርስቲያን ዶግማና ቀኖና ላይ ያተኮረ የወንጌል ትምህርት ተሰጥቷል፡፡

በተጨማሪም በሳጉሬ ቅድስት ሥላሴ፣ በአሰላ ደብረ ምጽላል ቅድስት ድንግል ማርያም፣ በደብረ ሰላም ቅዱስ ሚካኤል እንዲሁም በቅድስት ሥላሴ /ቤተ ሥላሴ/ ቤተ ክርስቲያናት ቅዳሜና እሑድ ከቅዳሴ በኋላ በማኅበረ ቅዱሳን መደበኛ መምህራን ለምእመናን ትምህርት ተሰጥቷል፡፡

 

በአገልግሎት ዙሪያ ያነጋገርናቸው ምእመናን በሰጡት አስተያየት እምነታቸውን ለማወቅና ለመረዳት እንዲሁም ከመናፍቃን Picture2የኑፋቄ ትምህርት ይጠበቁ ዘንድ የቤተ ክርስቲያን ዶግማና ቀኖና መሠረት ያደረገ ትምህርት በቀጣይነት እንዲሰጥ፤ እንዳይቋረጥባቸው ተማጽነዋል፡፡ “በሕፃንነቴ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ እሰማቸው የነበሩ መዝሙራትን እንዳስታውስ አደረገኝ፡፡ እባካችሁ እኛንም ልጆቻችንም ከዳንኪራ ባልተናነሰ በስመ መዝሙር ከሚቀርቡና ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ካልጠበቁ ጩኸቶች ታደጉን፡፡” ሲሉ በምሬት ገልጸዋል፡፡ በከፍተኛ ውዥንብር ውስጥ ይከታቸው የነበረው የያሬዳዊ ዜማ አቀራረብ የማኅበረ ቅዱሳን የመዝሙር ክፍል ያቀረበውን ከተመለከቱ በኋላ ትክክለኛውን የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሥርዓትና ትውፊት የጠበቁትን ለመለየት እንደረዳቸውና ማኅበረ ቅዱሳን እየሰጠ ባለው አገልግሎት መደሰታቸውን ገልጸዋል፡፡ “የማኅበረ ቅዱሳን ዘማርያን በሚዘምሩበት ወቅት በተለይ ሴቶች እኅቶቻችን ሲዘመሩ የሙሴ እኅት ማርያም እስራኤላውያን ባህረ ኤርትራን በተሻገሩበት ወቅት ከበሮ ይዛ እግዚአብሔርን ያመሰገኘችበት ዝማሬ አስታወሰኝ፡፡ ሰናይ እገሪሆሙ ለእለ ይእዜኑ ሰናየ ዜና /ኢሳ.52 እንዲል የምሥራች የሚናገሩ ሰዎች እግሮች አመጣጥ መልካም ነው፡፡ መልካም ዜና የሚናገሩ ናቸውና፡፡”በማለት በአገልግሎቱ በመደሰት አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡በተጨማሪም ከየማዕከላቱ የማኅበረ ቅዱሳን አባላት ጋር ሰፋ ያለ ውይይት ተደርጓል፡፡

 

በሐገረ ስብከቱ 27 ወረዳዎች ውስጥ 500 ቤተ ክርስቲያናት የሚገኙ ሲሆን ማኅበረ ቅዱሳን በሁሉም ወረዳዎች በመንቀሳቀስ 15 የወረዳ ማእከላት 11 የግንኙነት ጣቢያዎችና 1 ልዩ ማእከል በማቋቋም ቤተ ክርስቲያንን በማገልገል ላይ ይገኛል፡፡

በማኅበረ ቅዱሳን የተካሔደው ሐዋርያዊ የአገልግሎት መርሐ ግብር ኅዳር 29/2004 ተጀመሮ በ6 ወረዳዎችና በአሰላ ከተማ አከናውኖ ታኅሣሥ 10/2004 ዓ.ም በማጠናቀቅ ወደ አዲስ አበባ የተመለሰ ሲሆን በአጠቃላይ ከ20000 በላይ ምእመናን በመርሐ ግብሩ ላይ በመገኘት ተከታትለዋል፡፡

Sebe

ሕንፃ ሰብእ ወይስ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ይቀድማል?

ታኅሣሥ 16/2004 ዓ.ም

ትርጉም፡- በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ

 

Sebe

“የጌታን ቤት በወርቅ ወይም በብር ባለማስጌጣቸው ከጌታ ዘንድ በሰዎች ላይ የሚመጣ አንዳች ቅጣት የለም”


ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በማቴ.14፥23 ያለውን ንባብ በተረጎመበት ድርሳኑ ከሰው የሚቀርብላቸው ከንቱ ውዳሴን ሽተው ሕንፃ ቤተ ክርስቲያንን ሲያስጌጡ የሚታዩ ነገር ግን እንደ አልዓዛር ከደጃቸው የወደቀውን ተርቦና ታርዞ አልባሽና አጉራሽ ሽቶ ያለውን ደሃ ገላምጠው የሚያልፉትን ሰዎች ይገሥፃል፡፡ በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ዘመን አንዳንድ ባለጠጎች ደሃ ወገናቸውን ዘንግተው ከእግዚአብሔር ዋጋ የሚያገኙ መስሎአቸው ቤተ ክርስቲያንን የወርቅና የብር ማከማቻና መመስገኛቸው አድርገዋት ነበር፡፡ ይህ ጥፋት በአሁኑ ጊዜ መልኩን ቀይሮ በሕንፃ ኮሚቴ ሰበብ ምዕመኑን ዘርፎ የራሳን ሀብት ማከማቸት በአደባባይ የሚሰማና የሚታይ ምሥጢር  እየሆነ ነው፡፡ እነዚህን በዮሐንስ አፈወርቅ ዘመን ከተነሡት ጋር ስናነጻጽራቸው እነዚያ ከእነዚህ በጣም ተሸለው እናገኛቸዋል፡፡ ነገር ግን ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እነዚያን እንዴት ብሎ እንደሚወቅሳቸው እንመልከትና በዚህ ዘመን የሚፈጸመው ዐይን ያወጣ ዘረፋ ምን ያህል አስከፊ ቅጣትን ሊያመጣ እንደሚችል እናስተውለው፡፡

… ሰው ወላጆቻቸውን በሞት ያጡ ሕፃናትንንና ረዳት ያጡ ባልቴቶችን ከልብስ አራቁቶ በወርቅ የተለበጠ ጽዋ ለቤተ ክርስቲያን በማበርከቱ ብቻ የሚድን እንዳይመስለው ይጠንቀቅ፡፡ የጌታን ማዕድ ማክበር ከፈለግህ ስለእርሷ የተሠዋላትን ነፍስህን ከወርቅ ይልቅ ንጹሕ በማድረግ በእርሱ ፊት መባዕ አድርገህ አቅርባት፡፡ ነፍስህ በኃጢአት ረክሳና ጎስቁላ አንተ ለእርሱ የወርቅ ጽዋ በማግባትህ አንዳች የምታገኘው በረከት ያለ አይምሰልህ፡፡ ስለዚህም በወርቅ የተሠሩ ንዋያተ ቅድሳትን መስጠት የእኛ ተቀዳሚ ተግባር አይሁን፡፡ ነገር ግን የምናደርገውን ሁሉ በቅንነት እናድርግ እንዲህ ከሆነ ከእግዚአብሔር የምናገኘው ዋጋ ታላቅ ይሆንልናል፡፡ ሥራችንን በቅንነት መሥራታችን ከወርቅ ይልቅ እጅግ የከበረ ዋጋ አለው፤ እንዲህ በማድረጋችንም ከቅጣት እናመልጣለን፡፡

 

ቤተ ክርስቲያን የወርቅና የብር ማምረቻ /ፋብሪካ/ ወይም ማከማቻ አይደለችም፡፡ ነገር ግን የመላእክት ጉባኤ እንጂ፡፡ ስለዚህም የነፍሳችንን ቅድስና እንያዝ አምላካችንም ከእኛ የሚፈልገው ይኼንኑ ነው፡፡ ስጦታችን ከነፍሳችን ይልቅ አይከብርም፡፡

 

 

ጌታችን ከሐዋርያት ጋር በማዕድ በተቀመጠ ጊዜ ሥጋውን በብር ዳሕል ደሙንም በወርቅ ጽዋ አድርጎ አልነበረም ያቀረበላቸው፡፡ ነገር ግን በማዕዱ የነበሩት ንዋያተ ቅድሳት ሁሉ እጅግ የከበሩና ማዕዱም ታላቅ ነበር፡፡ ምክንያቱም ማዕዱ ሲቀርብ ሐዋርያት በመንፈስ ነበሩና፡፡ ለጌታችን ቅዱስ ሥጋና ደም ተገቢውን ክብር መስጠት ትሻለህን? አስቀድመህ ደሃ ወገንህን አስበው፥ መግበው፥ አልብሰው፥ የሚገባውን ሁሉ አድርግለት፡፡ እንዲህ ስል ቅዱስ ሥጋውን አታክብረው ማለቴ አለመሆኑን ልትረዳኝ ይገባሃል፡፡ አንተ በዚህ ማዕድ ቅዱስ ሥጋውን በሐር ጨርቅ በመክደንህ ያከበርከው ይመስልሃል፡፡ ነገር ግን ይህን አካል /ቅዱስ ሥጋውን/ በሌላ መንገድ አራቁተኸዋል፤ ለብርድም አጋልጠኸዋል፡፡ጌታችን ኅብስቱን አንሥቶ “ይህ ሥጋዬ ነው” ሲለን “ስራብ አላበላችሁኝም ስጠማ አላጠጣችሁኝም” ያለው አካሉን አይደለምን? ስለዚህም ጌታችን “እውነት እላችኋለሁ ከሁሉ ከሚያንሱት ከእነዚህ ለአንዱ ስላላደረጋችሁ ለእኔም አላደረጋችሁትም” በማለትም ጨምሮ አስተማረን፡፡

ድሆች ወገኖቻችን ለመኖር የሚያስችላቸውን መሠረታዊ የሆኑ ፍላጎቶቻቸውን ሁሉ ልናደርግላቸው ይገባናል፡፡ ይህን ማድረግ ቅድሚያ ልንሰጠው የሚገባን ግዴታችን ነው፡፡ በዚህ መልክ ክርስቶስ ኢየሱስ ከእኛ እንደሚሻው በመሆን ሕይወታችንን ቅዱስ በማድረግ ወደ ማዕዱ እንቅረብ፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እግሩን ሊያጥበው በቀረበ ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ “እግሬን በአንተ ልታጠብ አይገባኝም” በማለት ተከላክሎት ነበር፡፡ ነገር ግን ቅዱስ ጴጥሮስ የእርሱ መከላከል ከአክብሮት ይልቅ ታላቅ በረከትን ሊያሳጣው የሚችል መከላከል እንደሆነ አልተረዳም ነበር፡፡ ቢሆንም ከጌታ ዘንድ “ካላጠብሁህ ከእኔ ጋር ዕድል የለህም” የሚለውን ቃል ሲሰማ እርሱ ያሰበው ነገር ተገቢ እንዳልነበረ ተረዳ፡፡ እንዲሁ እኛም እንደታዘዝነው ለድሆች ወገኖቻችን ቸርነትን እናድርግ፤ እርሱን ማክበራችንም የሚረጋገጠው በፍቅረ ቢጽ እንጂ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያንን በማስጌጥ አይደለም፡፡ እግዚአብሔር በወርቅ ሳይሆን ከወርቅ ይልቅ ንጽሕት በሆነች ነፍስ ደስ ይሰኛልና፡፡ እንዲህ ስል ግን ስጦታዎችን ወደ እግዚአብሔር ቤት እንዳታምጡ ማለቴ እንዳልሆነ ልትረዱኝ እፈልጋለሁ፡፡ ነገር ግን ከስጦታዎቻችሁ በፊት ትእዛዙን መፈጸም ይቀድማል፡፡

በእርግጥ በተሰበረ ልብ ሆናችሁ ስጦታዎችን ወደ እግዚአብሔር ቤት ብታመጡ እርሱ አይባርካችሁም እያልኩ አይደለም ፡፡ ነገር ግን ድሆችን ከረዳችሁ በኋላ ስጦታን ለእርሱ ብታቀርቡ ታላቅ ዋጋን ታገኛለችሁ፡፡  በዚያኛው ስጦታ አቅራቢው ብቻ ተጠቃሚ ይሆናል፡፡ በዚህኛው ግን ቸርነትን የተደረገለት ወገንም ተጠቃሚ ይሆናል፡፡ አንድም የወርቅና የብር ዕቃን ስጦታዎች ማድረጋችን ከሰዎች ምስጋናን ለማግኘት ብለን የፈጸምነው ሊሆን ይችላል፡፡ በእርግጥም ደሃ ወገንህ ተርቦና ተጠምቶ እንዲሁም ታርዞ አንተ እንዲህ ማድረግህ ከዚህ ውጪ ሌላ ምክንያት የለውም፡፡ ደሃው ወገንህ በርሃብ እየማቀቀ አንተ የጌታን የማዕድ ጠረጴዛ በወርቅና በብር እቃዎች ብትሞላው ምንድን ነው ጥቅምህ? ነገር ግን አስቀድመህ ደሃውን አብላው አጠጣው እንዲሁም አልብሰው፡፡ በመቀጠል የጌታን ማዕድ (መንበሩን) በፈለግኸው መልክ በወርቅም ይሁን በብር አስጊጠው፡፡

ለድሃ ወገንህ ለጥሙ ጠብታ ታክል ቀዝቃዛ ውኃ እንኳ ሳትሰጠው የወርቅ ጽዋን ስጦታ አድርገህ ለእግዚአብሔር ታመጣለታለህን? እንዲህ ማድረግህ ጌታን ያስደስተዋልን? አካሉን የሚሸፍንበትን እራፊ ጨርቅ ለደሃ ወገንህ ነፍገኸው፣ መንበሩን በወርቅ ግምጃ ጨርቅ በማስጌጥህ ከጌታ ዘንድ የረባ ዋጋ አገኛለሁ ብለህ ታስባለህን? እንዲህ በማድረግ ጌታ አምላክህን በስጦታህ ልትሸነግለው ትፈልጋለህን? በዚህስ ድርጊትህ በአንተ ላይ የእግዚአብሔር ቁጣ አይነድምን? ወገንህ አካሉን የሚሸፍንበት እራፊ ጨርቅ አጥቶ በብርድ እየተጠበሰና በመንገድ ዳር ወድቆ የወገን ያለህ እያለ አንተ የቤተ ክርስቲያን ዐምዶች በወርቅ በመለበጥህ ጌታ በአንተ ደስ የሚለው ይመስልሃልን? ይህል ከባድ ኃጢአት አይደለምን?… ኦ እግዚኦ አድኅነነ እም ዘከመ ዝ ምግባር አኩይ!!