DSC01450

በስልጤና ሀድያ፣ ጉራጌ፣ ከንባታ ሀገረ ስብከት በፖሊሶች የፈረሰው የጋራሬ ቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያን በአክራሪ ሙስሊሞች ፍርስራሹ ተቃጠለ፡፡

ኅዳር 21/2004 ዓ.ም

በዲ/ን ኅሩይ ባዬ

፠በቃጠሎው ወንጀል የስልጤ ቲትጎራ 1ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት እና የስልጢ 2ኛ ደረጃ ተማሪዎች ተሳትፍበውታል፡፡
፠የስልጢ አረጋውያን ሙስሊሞች ድርጊቱን ተቃውመዋል፡፡

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በስልጤና ሀድያ፣ ጉራጌ፣ ከንባታ ሀገረ ስብከት በስልጤ ደብረ ስብሐት ቅድስት ማርያምና ቆቶ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ስር የተመሠረተው የጋራሬ ቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያን ኅዳር 19 ቀን 2004 ዓ.ም ረፋድ ላይ በአክራሪ ሙስሊሞች ሙሉ ለሙሉ መቃጠሉን ለመረዳት ተችሏል፡፡

DSC01450

የቤተ ክርስቲያኑ መቃጠል እንደተሰማ የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስና የማኅበረ ቅዱሳን ልዑካን በቦታው ተገኝተዋል፡፡ ብፁዕነታቸው ወደ ስልጢ ከመሔዳቸው በፊት በቡታጅራ ከተማ ተገኝተው በቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን የማጽናኛ መልእክት በማስተላለፍ የቡታ ጅራ ሕዝበ ክርስቲያን እንዲረጋጋ አድርገዋል፡፡

ቤተ ክርስቲያኑ ለምንና እንዴት እንደተቃጠለ ለማጣራት የደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልላዊ መንግሥት የጸጥታ አስተዳዳር ምክትል ሓላፊ አቶ ኢዮብ አንበሳ፣ የክልሉ ርእሰ መስተዳድር አማካሪ አቶ ፋሲል ጌታቸውና የክልሉ የጸጥታ ዘርፍ የሥራ ሒደት ሓላፊ አቶ በረከት ጌኤ  ተገኝተዋል፡፡

ቤተ ክርስቲያኑ እንዲቃጠል ከፍተኛውን ድርሻ ወስደው ተማሪዎችን ሲቀሰቅሱ የነበሩ በስም የሚታወቁ ግለሰቦችና አክራሪ ሙስሊሞች እንደሆኑ ተገንዝበናል፡፡ የወረዳው አስተዳደር ጽ/ቤት ወንጀሉ እንዳይፈጸም የቅድሚያ ዝግጅት ለምን እንዳላደረገ ለቀረበለት ጥያቄ እንደ መንግሥት አስተዳደር በሃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ መግባት ስለሌለብን ነው የሚል ምላሽ ሰጥቷል፡፡ በሃይማኖት ጉዳይ የመንግሥት ጣልቃ ገብነት እስከ የት እንደሆነ በግልጽ ማብራራት ያልቻሉት የስልጤ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ሐያቱ ሙክታር “የተቃጠለው ቤተ ክርስቲያን አይደለም” የሚል ማስተባበያ ለመስጠት መሞከራቸውን አረጋግጠናል፡፡ ሆኖም የተቃጠለው ቤተ ክርስቲያን ለመሆኑ የፎቶግራፍ ማስረጃ ለክልሉ ባለስልጣናት ሊቀ ጳጳሱ አቅርበዋል፡፡ ዜጎች በሀገራቸው ተከባብረው፣ ተፈቃቅረው ለሰላም       ለልማትና ለእድገት በሚተጉበት በዚህ ወቅት መንግሥት ባለበት ከተማ እንዲህ ያለ ወንጀል መፈጸሙ ያሳዘናቸው ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ ወንጀሉን የፈጸሙ አካላትን ጉዳይ ለፍርድ የማቅረቡን ሒደት ከሚመለከታቸው የበላይ የመንግሥት አካላት ጋር በመወያየት ላይ መሆናቸውን አስታውቀዋል፡፡

ተማሪዎች ከትምህርት ገበታቸው ወጥተው ቤተ ክርስቲያንን ለማቃጠል ያነሣሣቸውን አካል በሕግ መጠየቅ እንዳለበት ያብራሩት የክልሉ የጸጥታ አስተዳዳሪም የሕዝበ ክርስቲያኑን ትእግሥት አድንቀዋል፡፡

ኅዳር 19 ቀን 2004 ዓ.ም አመሻሽ ላይ የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ፣ የስልጢ ከተማ ምእመናንና የክልሉ የመንግሥት ባለሥልጣናት በተገኙበት ከ25 እስከ 30 የሚሆኑ የምእመናን ተወካዮች ተመርጠው ከሚመለከታቸው የሕግ አካላት ጋር ወንጀለኞችን ለማጋለጥ የማጣራቱ ሒደት ቀጥሏል፡፡

ዛሬ በደረሰን መረጃ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስና የመንግሥት ባለሥልጣናት በተገኙበት በምእመናን የተመረጡ ከ25 እስከ 30 የሚሆኑ ሽማግሌዎች ሥራቸውን እንዳይጀምሩ እየተደረገ ነው፡፡ በተለይ ከ1938 ዓ.ም ጀምሮ የደብረ ስብሐት ቅድስት ማርያምና ቆቶ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ለጥምቀተ ባሕር የሚጠቀሙበት ቦታ ለሌላ አገልግሎት መዋል የለበትም የሚል አቤቱታ ሲያቀርቡ የነበሩ ካህናት በኮሚቴ ውስጥ ቢመረጡም ሥራቸውን መቀጠል አልቻሉም፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ጉዳዩን በደንብ የማያውቁት ሰዎች እንዲተኩ መደረጋቸው የችግሩን መንስኤና ዘለቄታዊ መፍትሔ ለማግኘት አጠራጣሪ እንደሆነ የአካባቢው ምእመናን ጠቁመዋል፡፡

 

ኅዳር 19 ቀን 2004 ዓ.ም የቤተ ክርስቲያኑን መፍረስ የዘገብን መሆኑ ይታወቃል፡፡ የቃጠሎውን ተግባር የፈጸሙት በእድሜ ያልበሰሉ ሕፃናት ናቸው ተብሎ ወንጀሉ እንዲዳፈን መደረጉ እንዳሳዘናቸው የስልጢ ምእመናን እያሳሰቡ ነው፡፡

DSC00379

በስልጤና ሀድያ ጉራጌ ሀገረ ስብከት የጋራሬ ቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያን በወረዳው ፓሊስ አባላት እንዲፈርስ መደረጉ ተገለጠ፡፡

ኅዳር 19/2004 ዓ.ም

በዲ/ን ኅሩይ ባዬ

•    ቤተ ክርስቲያኑ የፈረሰው እኩለ ሌሊት እንደሆነም ታውቋል፡፡
•    የስልጢ 2ኛ ከፍተኛ ደረጃ ተማሪዎች በቤተ ክርስቲያኑ መፍረስ እንዲተባበሩ እየተቀሰቀሱ ነው፡፡

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በስልጤና ሀድያ ሀገረ ስብከት በስልጤ የጋራሬ ቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያን ኅዳር 15 ቀን 2004 ዓ.ም ዓርብ ለቅዳሜ አጥቢያ እኩለ ሌሊት ላይ በወረዳው የፓሊስ አባላት የመፍረስ አደጋ እንደተጣለበት ከክልሉ የደረሰን ማስረጃ አረጋገጠ፡፡

በስልጤ ዞን በስልጢ ወረዳ በቆቶ ባለሦ ቀበሌ በቆቶ መንደር በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስም የይዞታ ቦታው በሰነድ እንዲረጋገጥ የደብሩ ሰበካ ጉባኤ ለደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልላዊ መንግሥት ለግብርና ገጠር ልማት ቢሮ ለተፈጥሮ ሀብትና የገጠር መሬት አስተዳደር ዘርፍ ባቀረበው ጥያቄ አግባብነት ያለው የመንግሥት የሥልጣን አካል በቀን 15/04/2003 ዓ.ም የይዞታ ማረጋገጫ ሰነዱን ለደብሩ ሰበካ ጉባኤ መስጠቱን መረጃዎች ያስረዳሉ፡፡

DSC00379

በተሰጠው የይዞታ ቦታ ተደጋጋሚ የሆነ ክስ ይቀርብ እንደነበር የሚገልጡት የወረዳው ምእመናን የተፈቀደው ቦታ ለጥምቀተ ባሕር በመሆን ማንኛውም የእምነት ተከታይ አምልኮውን ሊፈጽም እንደሚችል በተቃራኒ ወገን አቤቱታዎች መቅረባቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡ ሆኖም ከወረዳው ፍርድ ቤት እስከ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ድረስ ጉዳዩ በተደጋጋሚ ታይቶ የቤተ ክርስቲያኑ አገልግሎት በተፈቀደለት ቦታ መንፈሳዊ ሥራውን እንዲቀጥል በመዝገብ ቁጥር 05681 የተወሰነውን ውሳኔ በመጥቀስ የወረዳው ፍርድ ቤት በቀን 13/12/2003 ዓ.ም ከፍተኛ ፍርድ ቤቱ ደግሞ በቁጥር 16/507/23/205 በቀን 13/04/2003 ዓ.ም ባስተላለፈው ትእዛዝ አስታወቋል፡፡

የሕግ አግባብ ባለው መሥሪያ ቤት ተፈቅዶ መሠረቱ ተቀምጦ የተሠራው ቤተ ክርስቲያን ድንገት በመፍረሱ የተደናገጡት የስልጢ ምእመናን ጉዳዩን ለሚመለከተው የበላይ አካል ለማቅረብ ወደ ሐዋሳ አስተዳደር ጽ/ቤት በቀን 18/03/2004 ዓ.ም ጉዞአቸውን አቅንተዋል፡፡ በእለቱም የክልሉ የጸጥታና አስተዳደር ቢሮ የምእመናኑ አቤቱታ አግባብነት ያለው በመሆኑ አጣሪ ኃይል ወደ ቦታው እንደሚላክ ምላሽ እንደተሰጣቸው ተገልጧል፡፡

ኅዳር 19 ቀን 2004 ዓ.ም የደረሰን መረጃ እንደሚያመለክተው በስልጢ ከተማ ጥቂት አክራሪ ሙስሊሞች በሙስሊምና በክርስቲያኑ መካከል ግጭት እንዲፈጠር ቅስቀሳ እያደረጉ ነው፡፡ ከዚህም በተያያዘ በስልጢ ከተማ 1ኛ እና ከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት የሚማሩ ተማሪዎች ቤተ ክርስቲያኑ እንዲፈርስ የሚደረገውን ተግባር እንዲፈጽሙ መቀስቀሳቸውንና ተማሪዎቹ ተሰባስበው ወደ ቤተ ክርስቲያኑ በመሔድ ነዳጅ ጨምረው ቤተ ክርስቲያኑን ሙሉ በሙሉ ማቃጠላቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡

የስልጢ ምእመናን በሕግ ተፈቅዶ በተሰጣቸው ቦታ ቤተ ክርስቲያን ሠርተው መገልገል ሊጀምሩ በተዘጋጁበት ወቅት ሕጋዊ ነኝ በሚል የፖሊስ አካል በመንፈቀ ሌሊት እንዲፈርስ መደረጉና በሕገ ወጥ ወጣቶች እንዲቃጠል መደረጉ እንዳሳዘናቸው አብራርተዋል፡፡

ቀጣዩ ሒደት እንደደረሰን የምናሳውቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡

የሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት ያስገነባው ሕንፃ ተመረቀ

ዲ/ን ቴዎድሮስ ኃይሉ

•    የብፁዕ አቡነ ቄርሎስ 25ኛ ዓመት የብር እዩቤልዩ በዓልም ተያይዞ ተከብሯል

{gallery count=1 width=350 height=300 counter=1 links=0 alignment=center animation=3000}abunekerilos{/gallery}

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን የሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት ያስገነባው ባለ ሁለት ፎቅ ሁለገብ ሕንፃ፤ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ተወካዮች፣ የመንግሥት አመራር አካላት፣ የአድባራትና የገዳማት አስተዳዳሪዎች እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት ህዳር 10/2004 ዓ.ም የደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በብፁዕ አቡነ አትናቴዎስና በአቶ ሓየሎም ጣውዬ የወልድያ ከተማ ከንቲባ ተመረቀ፡፡

 

መልአከ ሐይል ስጦታው ሞላ በሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት የሰበካ ጉባኤ ማደራጃ ክፍል ኃላፊ  የአዳጎ ሕንፃ መሠራቱ ቤተ ክርስቲያኒቱ በስብከተ ወንጌል የምታደርገውን እንቅስቃሴ በጉልህ የሚደግፍ ነው ብለዋል ፡፡ የወልድያ ከተማ ከንቲባ አቶ ሓየሎም ጣውዬ በምረቃው ወቅት ‹‹ የሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት ሕዝቡን በእምነቱ የጸና፣ ሀገር ወዳድና በልማት ዋነኛ ተሳታፊ ለማድረግ እያከናወናቸው ያለው አበረታች የልማት ተግባራት መንግሥት ከያዛቸው የድኅነት ማስወገጃ ስትራቴጂዎች አንፃር የሚሄዱ ለመሆናቸው ምስክርነት የሚያሻው ጉዳይ አይደለም፡፡ ሀገረ ስብከቱ ከጀመራቸው የልማት ሥራዎች መካከል የወልድያ ከተማችን የኢንቬስትመንት እድገት የሚያሠራውን አዳጎ ላይ የተገነባው ሕንፃ ለሌሎችም አርአያ ከመሆን አልፎ ለብዙ ዜጎች የሥራ ዕድል ፈጥሮ ያለፈና አሁንም እየፈጠረ ያለነው ቢባል መጋነን አይሆንም ›› በማለት መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

 

ቦታው የሀገረ ስብከቱ ይዞታ በመሆኑ፣ በመሐል ከተማ ያለ ሆኖ ሕንፃው መገንባት ስላለበት እንዲሁም በመንግሥት አካላት በሕንፃ እንድትሰሩ እድሉ የእናንተ ነው ስለተባለ፤ ሕንፃውን ልንሠራ ችለናል በማለት መልአከ ሐይል ስጦታው ሞላ ተናግረዋል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን የሕንፃውን ፕላን በነጻ ሠርቶ መስጠቱ የሚያስመሰግነው ነው በማለትም አክለዋል ፡፡

 

ሀገረ ስብከቱ ያስገነባው አዳጎ ሕንፃ ባለሁለት ዘመናዊ ፎቅ ሲሆን ስድስት ሱቆች፤ አንድ ካፍቴሪያና ሬስቶራንት ፣ አንድ መለስተኛ አዳራሽ እና ሃያ ስድስት ለጽ/ቤት አገልግሎት የሚሰጡ ክፍሎች ያሉት ነው ፡፡ ሕንፃውን ለመሥራት ሁለት ዓመት የወሰደ ሲሆን በአጠቃላይም በ3.8 ሚሊዮን ብር ተጠናቋል፡፡

 

ከዚህ በፊት ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ ከበጎ አድራጊዎች ጠይቀው ባገኙት ከ300,000.00 ባላነሰ ወጪ የሀገረ ስብከቱ መንበረ ጵጵስና (ባለ አንድ ፎቅ ሕንፃ) እንዲሁም የካህናት ማሠልጠኛ በብር 260,000.00 መሠራቱ የሚታወስ ነው፡፡ ተያይዞም የብፁዕ አቡነ ቄርሎስ የሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ የቅዱስ ላሊበላ ደብር የበላይ ጠባቂና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል 25ኛ ዓመት የብር ኢዩቤልዩ በዓልም በደማቅ ሁኔታ ተከብሯል ፡፡

 

በሰሜን ወሎ ሀገረ ስበከት ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ ከመሾማቸው በፊት በወሎ ሀገረ ስብከት ሥር የነበረ መሆኑና ብፁዕነታቸው ከተሾሙ ጊዜ ጀምሮ ከህዳር ወር 1980 ዓ.ም ጀምሮ ከሀገረ ስብከቱ ባለመለየት በትጋት የወንጌል አገልግሎታቸውን እየተወጡ ያሉ አባት መሆናቸውን የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ መልአከ ገነት ዓለሙ አስማረ በወልድያ ከተማ ባህል አዳራሽ በተካሄደው ዝግጅት ተናግረዋል፡፡ ሥራ አስኪያጁ አያይዘው ብፁዕነታቸው ሊቀ ጳጳስ ሆነው ከተመደቡ ከ1980 ዓ.ም ጀምሮ ቀድሞ አንድ ብቻ የነበረውን ሰ/ት/ቤት አሁን ላይ አራት መቶ ሦስት መሆናቸውን ፣ አራት መቶ ሠላሳ አንድ  መምህራን መሰልጠናቸው፣ ከመቶ 20% ከብር 70,220.41 ወደ ብር 3,236,486.48 ማደጉን፣ በወረዳ ቤተ ክህነት ሠራተኞች ከሠላሳ አራት ወደ ሠባ ስድስት፣ ሀገረ ስብከቱ ሲመሰረት አምስት ሠራተኞች የነበሩ ሲሆን አሁን ሃያ ሁለት ሠራተኞች መጨመሩን፣ አጎራባች አህጉረ ስብከቶችን ሳይጨምር ለሀገረ ስብከቱ አገልጋዮች 7,618 የዲቁናና የቅስና ማዕረግ መስጠታቸውን፣ በምዕመናን ቁጥር በ173,791 ዕድገት መታየቱን፣ በወረዳ ደረጃ፣ በልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን በኩልና ሐዋርያዊ ጉዞ ያደረጉትን ግልጋሎት በሪፖርት አቅርበዋል፡፡

 

ከበዓሉ ታዳሚዎች ቅኔና መወድስ የቀረበ ሲሆን ምዕመናንም ለብፁዕነታቸው ረጅም የአገልግሎት ዕድሜን ከጤና ጋር እግዚአብሔር እንዲሰጣቸው ተመኝተዋል፡፡

 

ብፁዕነታቸው ያለባቸውን ከፍተኛ ሕመም በመቋቋም ለሠሩት ሥራም ከልዮ ልዮ አካላት ሽልማቶች የተበረከተላቸው ሲሆን የሀገረ ስብከቱ ሠራተኞችም ሙሉ መቀዳሻ አልባስ፣ ቆብና የእጅ መስቀል እንዲሁም ጥና ሲሸልሙ፤ የቅዱስ ላሊበላ ደብር በበኩሉ በትረ ሙሴ አበርክቶላቸዋል፡፡ ተያይዞም በአዳጎ ሕንፃ  አስተዋጽኦ ላደረጉ ልዩ ልዩ አካላት የሽልማትና የምስክር ወረቀት ተሰጥቷል፡፡

 

በዕለቱም የብፁዕነታቸውን ከልጅነታቸው ጀምሮ እስከአሁን ድረስ ያለውን ሐዋርያዊ አገልግሎት የያዘ መጽሔት ለንባብ በቅቷል፡፡

 

ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ በብፁዕ አቡነ ተክለ ሃይማኖት እጅ ግንቦት 30/1979 ዓ.ም የበዓለ መንፈስ ቅዱስ ዕለት ከአምስት አባቶች ጋር ለጵጵስ  ሹመት የበቁ ሲሆን እንደተሾሙም የተመደቡት በሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት መሆኑ ይታወቃል፡፡ ብፁነታቸው በሰሜን ወሎና ዋግ ኽምራ አሁጉረ ሰብከት በዋናነት ያገለገሉና እያገለገሉ ያሉ ሲሆን በተጨማሪም የአሰብ፣ የደቡብ ወሎ እና የደቡብ ሸዋ ሀገረ ስብከትን በሊቀ ጵጵስና ደርበው እንዲሁም በ1986 ዓመተ ምሕረት በምሥራቅ ሸዋ ተዛውረው ለስምንት ወራት አገልግለዋል ፡፡

Aba Heruye

ማኅበረ ቅዱሳን ከአዲሱ የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሓላፊ ጋር ስለ ቀጣዩ የአገልግሎት ዘመን ተወያየ፡፡

ኅዳር 8/2004 ዓ.ም

በዲ/ን ኅሩይ ባየ

ማኅበረ ቅዱሳን ከአዲሱ የሰ/ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሓላፊ መልአከ ጽዮን ቆሞስ አባ ኅሩይ ጋር ኅዳር 7 ቀን 2004 ዓ.ም ስለ ቀጣዩ የአገልግሎት ዘመን ተወያየ፡፡
በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት በሰ/ት/ቤቶች ማደሪጃ መምሪያ ቢሮ በተደረገው ውይይት፣ ማኅበረ ቅዱሳን ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል የተነሣባቸውን ወደ ዐሥራ ሁለት የሚሆኑ ነጥቦችን በማብራራት የማኅበሩ ሰብሳቢ ሊቀ ትጉሃን ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ስዩም ንግግር ያደረጉ ሲሆን ለአዲሱ የመምሪያ ሓላፊ የማኅበሩን አጠቃላይ አሠራር በተሰጠው ሕግና መመሪያ መሠረት እንዲቆጣጠሩና በቅርብ እንዲከታተሉ ጨምረው ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡
Aba Heruye
መልአከ ጽዮን አባ ኅሩይም ከዐሥራ ሁለት ዓመት የውጭ ሀገር አገልግሎት በኋላ በፈቃደ እግዚአብሔር በቅዱስ ፖትርያርኩና በብፁዓን አባቶች ይሁንታ እንዲያገለግሉ ሲጠሩ ደስታ እንደተሰማቸው በመግለጥ፣ “የሰው ልጆች ጠባይ እንደ መልካችን የተለያየ ቢሆንም እንደ አመላችን ሰብስባ የያዘችን ቤተ ክርስቲያን ናት፣ የቤተ ክርስቲያናችን የአሠራር መንገዱ አንድ ነው፤ ስለዚህ የተገናኘነው በቤተ ክርስቲያንና ስለ ቤተ ክርስቲያን ስለሆነ በአባቶቻችን ጸሎት እየታገዝን እናገለግላለን” ብለዋል፡፡
በውይይቱ ላይ የተገኙት የከምባታ፣ ሀድያና ስልጤና ጉራጌ አህጉረ ስብከት እንዲሁም የሰ/ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ እንዳስታወቁት ማኅበረ ቅዱሳን ራሱን ደሴት አድርጎ ለብቻው የሚጓዝ ተቋም ሳይሆን በቤተ ክርስቲያን መዋቅር ውስጥ ያለ ማኅበር ነው፡፡ በመሆኑም በመደማመጥ እና በመወያየት ከሠራን ችግር አይኖርም፡፡ መለያየት ለጠላት ያመቻል፡፡ አንድ ከሆንን ግን ልዩነታችንን የሚፈልጉ ሰዎች መግቢያ አይኖራቸውም፤ ስለዚህ ለመልካም ነገር በሮቻችንን እየከፈትን ለመጥፎ ነገር ደጃችንን ልንዘጋ ይገባል ብለው፣ የምንሠራው ሥራ ውጤታማ የሚሆነው በመፈቃቀር፣ በመቀራረብ፣ በመወያየትና የቤተ ክርስቲያንን መዋቅር ጠብቀን ስንሠራ ነው በማለት አሳስበዋል፡፡
ብፁዕነታቸው አያይዘው መልአከ ጽዮን አባ ኅሩይን የተሰጣቸውን ትልቅ ሓላፊነት በእውነትና በሐቅ እንዲወጡ አባታዊ ምክር አስተላልፈዋል፡፡
በውይይቱ የማደራጃ መምሪያው ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ፣ የማደራጃ መምሪያው ኃላፊ መልአከ ጽዮን አባ ኅሩይ መሸሻ፣ የማኅበረ ቅዱሳን ሥራ አመራር ጉባኤ፣ ሥራ አስፈጻሚ፣ ኦዲትና ኢንስፔክሽን፣ የኢዲቶሪያል ቦርድ አባላትና የሚዲያ ክፍል አገልጋዮች እንዲሁም ልዩ ልዩ የማኅበሩ አባላት ተገኝተዋል፡፡
መልአከ ጽዮን አባ ኅሩይ ከሰ/ት/ቤት ወጣቶችና በሥራቸው ካሉ ማኅበራት ጋር ተግባብተው እና ተናበው አገልግሎታቸውን እንደሚወጡ ይጠበቃል፡፡

 

Dr_George_Tadros1

ግብጻውያን ኦርቶዶክሳዊ የሕክምና ባለሙዎች በኢትዮጵያ ነጻ አገልግሎት ሰጡ::

በኢዮብ ሥዩም

በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ጠያቂነትና በግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን መልካም ፈቃድ ግብጻውያን ኦርቶዶክሳዊ የሕክምና ባለሙያዎች በኢትዮጵያ ነጻ አገልግሎት ሰጡ፡፡

የሕክምና ቡድኑ አባላት ከ27/2/2004 ዓ.ም – 1/3/2004 ዓ.ም ድረስ በአዲስ አበባ ውስጥ በሚገኙ ሆስፒታሎች በተለያዩ የሙያ ዘርፎች አገልግሎትDr_George_Tadros1 እንደሰጡ ለማወቅ ተችሏል፡፡ ሃያ ሦስት አባላት ያሉት የሕክምና ቡድን አባላት መሪ የሆኑት ዶክተር ጆርጅ ታድሮስ እንደተናገሩት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን የአገልግሎት ጥሪ በቤተ ክርስቲያናቸው በኩል እንደደረሳቸው ሁሉም የተመረጡት ልዑካን ወደ ኢትዮጵያ ለመምጣት ሙሉ ፈቃደኛ ነበሩ፡፡

 

የሕክምና ቡድኑ አባላት መቀመጫቸው ሰሜን አሜሪካ፣ ካናዳ፣ እንግሊዝ ቢሆንም ቤተ ክርስቲያናቸው ለአገልግሎት በምትጠራቸው ወቅት ፈጣን ምላሽ ለመስጠት መምጣታቸውን አስረድተዋል፡፡በተለያዩ የዓለማዊ ሥራ ቦታ የተሰማሩ የኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ልጆች በሙያቸው ቤተ ክርስቲያንን ለማገዝ ሃይማኖት ሳይለዩ ለሕዝቦች ሁሉ ቀና ግልጋሎት ለመስጠት መትጋት እንደሚገባቸውም የቡድን መሪው ገልጸዋል፡፡

 

ቤተ ክርስቲያን የብዙኃን መጠጊያ ነች ያሉት የቡድን መሪው በኢትዮጵያ የግብጽ ኦርቶዶክሳዊ ሐኪሞች የሰጡት የሕክምና እርዳታ ወደፊት ከማኅበረ ቅዱሳንና ከመሰል የቤተ ክርስቲያን አካላትና ባለሙያዎች ጋር በመተባበር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል፡፡የልዑካን ቡድኑ አባላት በኢትዮጵያ ቆይታቸው የሕዝቡን ክርስቲያናዊ ፍቅር በነጻነት ሃይማኖቱን የመከተል እድልና እንግዳ ተቀባይነቱ እንዳስደሰታቸው ተናግረዋል፡፡

Arega_42_X_30_Ca__q100

የሰለሞን ምቅናይ ምስል ወድምጽ /ቪሲዲ/ ተመረቀ

ኅዳር 6/2004 ዓ.ም

በፈትለወርቅ ደስታ

Arega_42_X_30_Ca__q100በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ በሰ/ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን “የሰለሞን ምቅናይ በተክሌ ዝማሜ በሚል ርእስ የተዘጋጀ ምስል ወድምጽ /ቪሲዲ/ ቅዳሜ ኅዳር 2/2004 ዓ.ም በጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ ተመረቀ፡፡

በምረቃው ላይ ብፁዕ አቡነ ሰላማ የአክሱም ጽዮን ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ እንድርያስ የደቡብ ጐንደር ሊቀ ጳጳስና ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና ተጋባዥ እንግዶች ተገኝተዋል፡፡

የማኅበሩ ሰብሳቢ ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ስዩም በምረቃው ላይ የመክፈቻ ንግግር ያደረጉ ሲሆን ቤተ ክርስቲያን የራሷ የሆነውን የዜማ፣ የአቋቋም ሥርዓት ጠብቃ በእንዲህ ዓይነት መልኩ ለምእመናን እንዲዳረስ ማኅበሩ የበኩሉን ድርሻ እንደሚወጣና ወደፊትም ከዚህ በተሻለ መልኩ እንደሚሠራ ገልፀዋል፡፡ ብፁዕ አቡነ እንድርያስም በዕለቱ “ምቅናይ” በሚል ርዕስ ሰፋ ያለ ትምህርት ሰጥተዋል፡፡ አያይዘውም ይህ የቤተ ክርስቲያን ቅርስና ሀብት ዜማ ዝም ብሎ የተገኘ ሳይሆን ሊቃውንቱ እድሜያቸውን ሙሉ ሲማሩት የኖሩት መሆኑንና ይህን የቤተ ክርስቲያን ሀብት ደግሞ በእንዲህ ዓይነት መልኩ ለትውልድ የማስረከብ ኃላፊነት የሁሉም የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ልጆች ኃላፊነት መሆኑን ተናግረዋል፡፡

298135_242419749145401_100001321341150_593861_1645855864_n

በዕለቱ በየኔታ ተክሌ ሲራክ አማካይነት በተክሌ አቋቋምና ዝማሜ ታሪክ ላይ ጥናታዊ ጽሑፍ የቀረበ ሲሆን ይህ የተክሌ ዝማሜ በደብረ ታቦር ኢየሱስ ገዳም እስከ አሁን ድረስ የተክሌ አቋቋም ጉባኤ ምስክር ሆኖ እንደሚያገለግል ገልጸዋል፡፡

በመጨረሻም ብፁዕ አቡነ እንድርያስ ይህ ጅማሮ ጥሩ መሆኑን ገልፀው ይህ ዝማሜ የሊቃውንቱ ቢሆንም ለእይታ የበቃው በማኅበረ ቅዱሳን አማካይነት መሆኑና ማኅበሩም በዚህ ዙሪያ ከፍተኛ ኃላፊነትን ወስዶ የድርሻውን እየተወጣ እንደሆነ ገልጸው ነገር ግን ገና አልተነካም ወደፊት ብዙ ይጠበቃል ብለዋል፡፡

ቪሲዲው የተዘጋጀው በማኅበረ ቅዱሳን በሙያ አገልግሎት እና አቅም ማጎልበቻ  ክፍል ዘርፍ ፕሮጀክት ተጠንቶና ሊቃውንቱ መክረውበት ነው፡፡

ከትርፍ ነፃ የሆኑ የምስልና የድምጽ ሲዲዎች እንደሚሠራጩ ተገለጠ፡፡

በዲ/ን ኅሩይ ባየ
ቀን 05/03/2004ዓ.ም.

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን በኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ክፍል የተዘጋጁ 3 ሺህ የሚሆኑ የምስልና የድምጽ ሲዲዎች ኅዳር 8 ቀን 2004 ዓ.ም በማኅበሩ ጽ/ቤት እንደሚሠራጭ የምክረ ሐሳቡ አስተባባሪ ኢንጂነር ሙሉጌታ ጌትነት አስታወቁ፡፡

ኢንጅነር ሙሉጌታ እንደገለጡት የምስልና የድምጽ ሲዲዎችን ለማግኘትና ለማሠራጨት ምንም ዐይነት ትርፍ ታሳቢ ሳይደረግ የሲዲውን ዋጋ ብቻ በመሸፈን ማግኘት ይቻላል፡፡ በማያያዝም የሥርጭቱ ዋና ዓላማ ስብከተ ወንጌልን በተፋጠነ መንገድ ለምእመናን ማዳረስ ሲሆን በገበያ ላይ የሚገኙት የምስልና የድምጽ ሲዲዎች የምእመናንን ምጣኔ ሀብት የሚጎዱ በመሆናቸው በቀላሉ ቃለ እግዚአብሔር የሚስፋፋበትን መንገድ ለማመቻቸት፣ የተሐድሶ መናፍቃን ስሑት ትምህርቶች በሕዝበ ክርስቲያኑ ሰርገው ስለገቡ ትክክለኛ ኦርቶዶክሳዊ አስተምህሮ ያላቸውን የስብከት ሲዲዎች ምእመናን እንዲያገኙና ስለ ሃይማኖታቸው እንዲያውቁ ለመደገፍ፣ በከተማ የሚኖሩ ጥቂት ምእመናን የመካነ ድር አገልግሎት ተጠቃሚዎች ቢሆኑም አገልግሎቱ ውድና ዝቅተኛ ፍጥነት ስላለው የምስልና የድምጽ ዝግጅቶችን መመልከትና መስማት ስለማይችሉ ችግሩን አስወግዶ ተደራሽነትን ለማስፋፋት እንዲቻልና የቪሲዲ አገልግሎት ከገጠር እስከ ከተማ እየተስፋፋ በመምጣቱ ንጹህ የቤተ ክርስቲያን ትምህርቶችን ለሁሉም እንዲዳረስ ለማድረግ እንደሆነ አስተባባሪው አስገንዝበዋል፡፡

ስርጭቱ እስከ ሦስት ዙር የሚቀጥል ሲሆን በመጀመሪያው ዙር ለአዲስ አበባ ምእመናን ይከፋፈላል፡፡ በሁለተኛውና በሦስተኛው ዙር የሚከናወኑት ስርጭቶች ደግሞ ከአዲስ አበባ ውጭ ወደ ማእከላትና ግንኙነት ጣቢያዎች እንደሚላኩ ለማወቅ ተችሏል፡፡ ስርጭቱን በተመለከተ ራሱን የቻለ ኮሚቴ እንደተዋቀረም ተጠቁሟል፡፡

የምስልና የድምጽ ትምህርቶች የተዘጋጁት በማኅበረ ቅዱሳን የምስልና የድምጽ ክምችት ክፍል በተለያዩ ዘመናት የተቀረጹ የሊቃውንት ትምህርቶች፣ በኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ክፍል በተለያዩ መርሐ ግብሮች የተቀረጹና በአዲስ አበባ ራጉኤል ቤተ ክርስቲያን ሰ/ት/ቤት የተቀረጹ ትምህርቶች እንደሆኑ ተገልጧል፡፡ ዝግጅቱ ከትርፍ ነፃ በሆነ መልኩ ተዘጋጅቶ የሚሠራጭ በመሆኑ ምእመናን በቀላሉ እንዲጠቀሙበት ማኅበሩ ጥሪውን ያስተላልፋል ሲሉ አስተባባሪው አሳስበዋል፡፡

VCD-Advertisment

ታላቅ የቪሲዲ ምርቃት

አዘጋጅ፡- በኢ/ኦ/ተ/ቤተ ክርስቲያን ሰ/ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን ሙያ  አገልግሎትና አቅም ማጎልበቻ ዋና ክፍል
ቦታ፡-ጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ
ሰዓት፡- ቅዳሜ ኅዳር 02/03/2004 ዓ.ም ከቀኑ 7፡30 ጀምሮ

 

VCD-Advertisment

commitiee

30ኛው አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ተጀመረ

{gallery count=1 width=350 height=300 counter=1 links=0 alignment=center animation=3000}smg30{/gallery}

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን 30ኛው መደበኛ መንፈሳዊ ጉባኤ ጥቅምት 7 ቀን 2004 ዓ.ም በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የስብከተ ወንጌል አዳራሽ ከጠዋቱ 3 ሰዓት በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ጸሎተ ቡራኬ ተጀምሯል፡፡

 

የ48ቱ አህጉረ ስብከት ሊቃነ ጳጳሳት በከፊል የተገኙ ሲሆን ሁሉም የሀገር ውስጥ ሥራ አስኪያጆች ፣የመንበረ ፓትሪያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የመምሪያ ሓላፊዎች ፣በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገር የሚገኙ የአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎች ፣ በኢትዮጵያ የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልዕኮ መምሪያ ፣ የሕፃናትና ቤተሰብ ጉዳይ ድርጅት፣ የልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን ሓላፊዎች የጉባኤው ተሳታፊዎች ናቸው።

የመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም ካህናት “ስምዐነ አምላክነ ወመድኃኒነ ተስፋሆሙ ለኩሎሙ አጽናፈ ምድር” የሚለው የዳዊት መዝሙር ተሰብኮ “በምድር የምታስሩት በሰማይ የታሰረ ይሆናል በምድርም የምትፈቱት በሰማይ የተፈታ ይሆናል፡፡…. ሁለት ወይም ሦስት በስሜ በሚሰበሰቡበት በዚያ በመካከላቸው እሆናለሁና” የሚለው የማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ 18 ቁጥር 18 በቅዱስነታቸው ተነቧል፡፡

 

ቅዱስነታቸው በጸሎተ ወንጌል ጉባኤውን ባርከው ከከፈቱ በኋላ በሰጡት ቃለ ምእዳን ሰው መግባባት የሚችለው እግዚአብሔር በሰጠው አእምሮ ሲጠቀምበትና በፈሪሃ እግዚአብሔር ሲኖር ነው። ፈሪሃ እግዚአብሔር ካለ ሰላም፣ ፍቅር፣ መግባባት፣ መዋደድና መከባበር ይኖራል ብለው በሰላማዊ መንገድ ሓላፊነትን መወጣት እንዲገባ አሳስበዋል፡፡

ቅዱስ ፓትርያርኩ አያይዘው በ2003 ዓ.ም በሞት የተለዩንን ብፁዕ አቡነ በርናባስን፣ ብፁዕ አቡነ ይስሐቅንና ብፁዕ አቡነ ሚካኤልን በጸሎት እናስባቸው ብለው ጸሎት አድርሰዋል፡፡

 

ሊቀትጉሃን ኃይለ ጊዮርጊስ ዳኜ፣ መጋቤ ሰናያት አሰፋ ስዩም፣ ሊቀ ስዩማን ራደ አስረስ፣ ንቡረ እድ ተስፋዬ ተወልደና መጋቤ ሐዲስ ይልማ ቸርነት የአቋም መግለጫ ረቂቅ እንዲያዘጋጁ ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ ለጉባኤው አቅርበው ጉባኤው የተመረጡትን አርቃቂዎች በሙሉ ድምጽ አሳልፈዋል፡፡commitiee

 

ከረፋዱ 4 ሰዓት ጀምሮ ለ45 ደቂቃ ያህል የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት አጠቃላይ ሪፓርት በብፁዕ አቡነ ፊልጶስ የጠቅላይ ቤተ ክርህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የኢሉባቡርና ጋምቤላ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና በንቡረ እድ ኤልያስ አብርሃ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ምክትል ሥራ አስኪያጅ ቀርቧል፡፡ ከመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ሪፖርት ቀጥሎ የትግራይ ማዕከላዊ ዞን /አክሱም/ ሀገረ ስብከት ሪፖርት መቅረብ የነበረበት ቢሆንም የጋምቤላ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ ለሌላ ተልእኮ ወደ ሱዳን ሀገረ ስብከት መሔድ እንዲችሉ ፈቃድ ጠይቀው ቅድሚያ ሪፖርታቸውን አቅርበዋል፡፡

 

በጠዋቱ መርሃ ግብር የትግራይ ማዕከላዊ ዞን፣ የሲዳማ፣ የሰሜን ጎንደር፣ የምሥራቅ ሀረርጌ፣ ሀገረ ስብከት ሪፖርት ቀርቧል፡፡ ከሰዓት በኋላ በተያዘው መርሃ ግብር ከቀኑ 8 ሰዓት እስከ 11፡30 ድረስ የጅማ ዞን ሀገረ ስብከት፣ በትግራይ ክልል ሀገረ ስብከት የመቀሌ፣ የኢሊባቡር፣ የድሬዳዋ፣ የጋሞጎፋ፣ የሰሜን ወሎ፣ የባሌ፣ የደቡብ ጎንደርና የምሥራቅ ወለጋ አህጉረ ስብከት ሪፖርት ቀርቧል፡፡

 

ረቡዕ ጥቅምት 8 ቀን 2004 ዓ.ም ከጠዋቱ 3 እስከ 6፡30 በነበረው መርሐ ግብር የአርሲ፣ የትግራይ ምሥራቅ /አዲግራት/፣ የምዕራብ ጎጀም፣ የከፋ ቦንጋ፣ የሰሜን ሸዋ፣ የአሶሳና የደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት ሪፖርት ቀርቦ እንዳበቃ የቆሜ አቋቋም ሊቃውንት ወረብ አቅርበዋል፡፡

 

በሊቃውንቱ የቀረበው ወረብ እንደተጠናቀቀ የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ፣ የምሥራቅ ጎጃም፣ የምዕራብ ሐረርጌና የትግራይ ደቡባዊ ዞን /ማይጨው/ አህጉረ ስብከት ሪፖርት በንባብ ተሰምቷል፡፡

 

ከሰዓት በኋላ በተያዘው መርሃ ግብር የደቡብ ኦሞ፣ የሰሜን ምዕራብ ሸዋ የሰላሌ ሀገረ ስብከት የሐዲያና ስልጤ፣ የዋግ ሕምራ፣ የምዕራብ ሸዋ፣ የአፋር፣ የአዊ ዞን፣ የሶማሊያ፣ የምዕራብ ወለጋ፣ የትግራይ ሰሜናዊ ምዕራብ ዞን ሽሬ ሀገረ ስብከትና የትግራይ ሰሜናዊ ምዕራብ ዞን ሽሬ ሀገረ ስብከትና የጉራጌ ሀገረ ስብከት ሪፖርት ከቀረበ በኋላ ውይይት ተካሒዷል፡፡

 

30 ዓመት ያስቆጠረው የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ካሳለፈው ረዥም ጉዞ ጋር ሲነጻጸር የሚጠበቅበትን ውጤት እያስመዘገበ እንዳልሆነ በመንበረ ፖትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት የቀረበው ሪፓርት ያስረዳል፡፡

 

አጠቃላይ ጉባኤው እስከ ጥቅምት 11 ቀን 2004 ዓ.ም የሚቀጥል ሲሆን ለቤተ ክርስቲያን የሚጠቅሙ ውይይቶችና የውሳኔ ሐሳቦች እንደሚቀርቡበት ይጠበቃል፡፡

ቤተ ክርስቲያን የደረሰችበት ወቅታዊ ሁኔታ

ዲ/ን ታደሰ ወርቁ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰማያዊ ሥርዓት በምድር ያለች ሰማያዊት ተቋም ነች፡፡ በምድር ያለነውን ልጆቿን በሰማያዊው ሥርዓት በምድር አዘጋጅታ በሰማይ የምታኖር ናት፡፡ “አሐቲ” ተብላ የምትጠራ የክርስቲያኖች መገናኛ በመሆኗ ወደሷ ለሚመጣው ሁሉ በረኛ፣ ጥበቃ፣ ከልካይ፣ አሰናካይ የሌለባት ነፃ እልፍኛችን ናት፡፡ እንዲሁም ከበሉ መራብ፤ ከጠጡ መጠማት የሌለበት ሰማያዊውን መና፣ በሰማያዊ ሥርዓት የምታስገኝልን አማናዊ የእናት ጓዳ በመሆኗ መታመኛችንና መመኪያችን ናት፡፡
ከሁሉ ይልቅ ቤተ ክርስቲያን በማይነዋወጥ ወለድ ዋሕድ በሚለው መሠረተ እምነት፤ ነቢያት፣ ሐዋርያት ሊቃውንት ስለወልድ ዋሕድ በአስተማሩት ትምህርት መሠረት ላይ የታነፀች እውነተኛ የሕግና የትክክለኛ ሥርዓት መገኛ ናት፡፡ በየጊዜው የነበረው ፈተና የውስጥና የውጭ ጠላቶቿ ጥቃት አስተዳደራዊ ጉዞዋን ቅርቃር ውስጥ የከተተው ቢሆንም የዘመኑን ተልእኮዋን ለማሳካት በቂ ነበር፡፡
ይሁን እንጂ ቤተ ክርስቲያን አሐቲ፣ ሐዋርያዊት፣ ኩላዊት ሁና ሳለች በጥቂቶች ከላሽነት የተነሣ የውጭና የሀገር ውስጥ ሲኖዶስ በሚል ተከፋፍላለች፡፡ ተቋማዊ አስተዳደራዊ ፋይናንሳዊ ቀውስ ውስጥ ገብታለች፡፡ የዚህ ድምር ውጤትም የምእመናንን ሕሊናም እየከፈለ፣ እያደማም ይገኛል፡፡
ቤተ ክርስቲያን በአስተምህሮዋ በአስተዳደሯ፣ በፋይናንስ አያያዟና አጠቃቀሟ የከፋና ውስብስብ ጊዜ ጠየቅ ችግሮችና ፈተናዎች ተጋርጠውባታል፡፡ አንዳንዶቹ ፈተናዎችና ችግሮች ሥር የሰደዱ አዝማናትን ያስቆጠሩ ናቸው፡፡ አንዳንዶቹ ደግሞ ዘመንና መስክ ወለድ ናቸው፡፡ ሌሎቹ ደግሞ እንደ ቅዱሳት መጻሕፍት ከኅልፈተ ዓለም በፊት ይቆማሉ ተብሎ የሚታሰቡ አይደሉም፡፡ ቢያንስ ቢያንስ ግን ለዘመንና መስክ ወለድ ችግሮቻችን መፍትሔ ማፈላለግ የዘመናችን የቤተ ክርስቲያኒቱ ላአላይና ታህታይ መዋቅር መሪዎች ተናጥላዊና የወልዮሽ ሓላፊነት ነው፡፡
እናም በፈቃደ እግዚአብሔር፣ በአባቶቻችን የመንፈስ ልዕልናና ጽናት ተጠብቆ የቆየው የቤተ ክርስቲያኒቱ መሠረተ እምነት፣ ሥርዓተ አምልኮ፣ ትውፊት ለመጪው ትውልድ ያለ እንከን መተላለፍ የሚችለው፣ በጉልህ የሚታዩትን አስተምህሯዊ ቅሰጣ፣ የአስተዳደር፣ የፋይናንስ አያያዝና አጠቃቀም ችግሮችን ማረም፣ ማስተካከል፣ ሥርዓታዊና ሕጋዊ መሠረት ማበጀት ስንችል ብቻ ነው፡፡
ይህ ሆኖ እንድናይ ደግሞ በታሪክ መስታወትነት ወደ ኋላ ሔደን አሁን ያለንበትን ከአለፈው ጋራ በማዛመድ ከየት ተነሥተን ያለንበት ደረስን? ወዴትና በምን ያህል ፍጥነት እየመራን ነው? ምን ዓይነት የመፍትሔ አቅጣጫዎችን በምን ያህል ፍጥነት ብናስቀምጥ የተጋረጠብንን አደጋ እንቀንሳለን? ለሚሉት መሠረታዊ ጥያቄዎች ተግባራዊና ተጨባጭ ምላሽ መስጠት ያስፈልጋል፡፡
እነዚህን ሦስት መሠረታዊ እና የነባራዊው ሁኔታ ነጸብራቅ የሆኑትን ጥያቄዎች ከግንዛቤ በማስገባት ጽሑፉን በሦስት ዓበይት ክፍሎች ለማቅረብ መርጠናል፡፡ በመጀመሪያው ክፍል ቤተ ክርስቲያኒቱ እስከ አምስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ዘመናት በሚለው ርእስ ሥር ከየት ተነሥተን ያለንበት ደረስን? የሚለውን ጥያቄ ለመመለስ እንሞክራለን፡፡ በሁለተኛው ክፍል ደግሞ ቤተ ክርስቲያናችን አሁን ያለችበት ነባራዊ ሁኔታ በሚለው ርእስ ሥር ወዴትና በምን ያህል ፍጥነት እያመራን ነው? የሚለውን ጥያቄ ከምንገኝበት ነባራዊ ሁኔታ ጋር በማዛመድ ለማየት እንጥራለን፡፡ በሦስተኛውና የመጨረሻው ክፍል የመፍትሔ አቅጣጫ ጥቁምታ በሚለው ርእስ ሥር በሁለቱ ቀደምት ክፍሎች ትንታኔ ላይ በመመሥረት ምን ዓይነት የመፍትሔ አቅጣጫዎች፣ በምን ያህል ፍጥነት ብናስቀምጥ የተጋረጡብንን አደጋዎች እንቀንሳለን? የሚለውን ጥያቄ ለመመለስ እንሞክራለን፡፡

ቤተ ክርስቲያኒቱ እስከ አምስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን
ቤተ ክርስቲያኒቱ የነበረችበት ታሪካዊ ሁኔታ /Historical condition/ ጥርት ባለ እና በተስተካከለ ገጽታ ለመረዳት ተልእኮዋን እንደ አንድ ማንጸሪያ /parameter/ መጠቀሙ አስፈላጊ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ምድራዊውን ሰው በሰማያዊ ሥርዓት ወደ ሰማያዊ ኑሮ እንድታሸጋግር ከመሥራቿና ራሷ ከሆነው ክርስቶስ ሦስት መሠረታዊ ተልእኮ ተሰጥቷታል፡፡ በወልድ ዋሕድ መሠረተ እምነት ማጥመቅ፣ ማጽናትና መከታተል ናቸው፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ታሪካዊ ሁኔታ የምንፈትሸውም አንዱ ከእነዚሁ ተልእኮዎቿ ተነሥተን ነው፡፡

ቤተ ክርስቲያን በኢትዮጵያዊ ጃንደረባና በሶሪያዊው ፍሬምናጦስ ዘመን

ዶክተር ሥርግው ሐብለ ሥላሴ “The Religious Life In Ethiopia” በሚል ርእስ እ.ኤ.አ. በ1970 በአቀረቡት የጥናት ወረቀታቸው ላይ እንዳመለከቱት፣ የክርስትና ሃይማኖት ወደ ኢትዮጵያ የገባበት መንገድ ከሌላው ዓለም በእጅጉ ይለያል፡፡ በሌላው ዓለም ክርስትና የተጀመረው ከተርታው ሕዝብ ነው፡፡ በመንግሥት የታወቀና የተረዳ ሃይማኖት አልነበረም፡፡ በእኛ ሀገር ግን የመጀመሪያዎቹ አማኞች ከተርታው ሕዝብ አይደሉም፡፡ ነገሥታቱና መኳንንቱ ከነቤተሰቦቻቸው ነበሩ፡፡ ሃይማኖቱም ብሔራዊ ሃይማኖት ነበር፡፡ እንዲህ ዓይነቱ ክስተት በሌሎች የዓለም ሀገሮች የክርስትና ታሪክ ውስጥ አልሆነም፡፡ በኢትዮጵያ ግን ሆኗል፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ ክርስቲያን የሆነውም በዚህ ሁኔታ ነው፡፡
የክርስትና ሃይማኖት አገባብ ብቻ ሳይሆን የቤተ ክርስቲያኒቱም አደረጃጀት ከሌላው ዓለም እንዴት እንደሚለይ ዶክተር ሥርግው ሐብለ ሥላሴ በዚሁ የጥናት ወረቀታቸው ሲገልጹ፤ “…. የቤተ ክርስቲያኒቱ አደረጃጀትም ከሌላው የክርስትና ዓለም የተለየ ነበር፡፡ ክርስትናን ያስተዋወቀው የመጀመሪያ ሰው ሶሪያዊው ፍሬምናጦስ ነው፡፡ ይሁንና ከእርሱ በኋላ አስተዳደሩ ይመራ የነበረው በኢትዮጵያውያን አልነበረም፡፡ በግብጻውያን ጳጳሳት ሆኖ ቀጥሏል፡፡ ኢትዮጵያም በአንድ ጳጳስ ብቻ እንድትመራ በሕግ ደንግገዋል፡፡ በዚህ መልኩ ኢትዮጵያውያን ለአንድ ሺሕ ስድስት መቶ ዘመን በአንድ ግብጻዊ ጳጳስ ሥር እንዲወሰኑና ተጨማሪ አስተዳደራዊ ነፃነት እንዳይኖራቸው ተደርጓል” በማለት ነበር፡፡
በእርግጥ ክርስትናው የገባበት መንገድና የቤተ ክርስቲያኒቱ የአደረጃጀት መነሻ ከላይ የታሪክ ተመራማሪው ዶክተር ሥርግው እንደአስቀመጡት ቢሆንም ክርስትና ወደ ኢትዮጵያ የገባውና ወይም ኢትዮጵያና የክርስትና ሃይማኖት የተዋወቁት መጽሐፍ ቅዲስ እንደሚያስረዳው / ሐዋ.8፥26-40/ ሐዋርያው ፊልጶስ ኢትዮጵያዊውን ጃንደረባ ባጠመቀው ጊዜ ነው፡፡ ይህም የሆነው ከጌታ ልደት በኋላ በ34 ዓ.ም ነው፡፡
ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ የሸዋ ሊቀ ጳጳስ የነበሩት “የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ” በተባለው መጽሐፋቸው ከላይ በጠቀስነው አግባብ የኢትዮጵያና የክርስትና ሃይማኖት ትውውቅ ከአሰፈሩ በኋላ፣ በኢትዮጵያ ክርስትና ውስጥ የፍሬምናጦስ /አባ ሰላማን/ ሚና ሲገልጹ፤ “ኢትዮጵያዊው /ጃንደረባው/ ተጠምቆ ወደ ሀገሩ ከተመለሰ በኋላ አዲሱን ሃይማኖት ለሀገሩ ሕዝብ አስተምሯል፡፡ የመጀመሪያው የኢትዮጵያ ጳጳስ ፍሬምናጦስ /አባ ሰላማ/ ሥርዓተ ክርስትናን በትምህርት ያጠናከረው ኢትዮጵያዊው ጃንደረባ በመሠረተው ነው፡፡ ፍሬምናጦስ ጵጵስናውን ተቀብሎ ከተመለሰ በኋላ በኢትዮጵያ የክርስትናን ሥርዓት አስፋፈቶ ሰበከ፤ የክህነትና የቁርባንን ሕግ አጠናከረ፡፡ በኢትዮጵያ ግዛት በሙሉ የወንጌልን ትምህርት ለማዳረስ የሚረዱ ቀሳውስትንና ዲያቆናትን ሾመ፤ ቅዱሳት መጻሕፍትን ከሱርስት፣ ከዕብራይስጥና ከጽርእ ወደ ግእዝ ቋንቋ መለሰ፡፡ በዚህ አኳኋን በ330 ዓ.ም ክርስትና የኢትዮጵያ ብሔራዊ ሃይማኖት ሆነ” ይላሉ፡፡
ዲያቆን ዳንኤል ክብረት “የሐዋርያነት ሥራ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን አጭር መግቢያ” በሚለው የጥናት ወረቀቱ እንዳመለከተው ኢትዮጵያዊው ጀንደረባ ከአክሱም ቀጥሎ ኑብያን፣ ከኑብያም በኋላ ቀይ ባሕርን ተሻግሮ በየመንና በፐርሽያ ወንጌልን ሰብኳል፡፡
ከእርሱም በኋላ ደግሞ በአራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን አንድ ሊቅ በአምስተኛ መቶ ክፍለ ዘመን በሊቢያ የኢትዮጵያን ሰዎች ማየቱን ገልጧል፡፡ በአቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን ዘመንም አባታችን ወደ ኑብያ፣ አኑኖ እና መርዌ አምስት ቆሞሳትን ልከው እንደነበረ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ አብርሃና አጽብሐ ክርስትናን ተቀብለው ከተጠመቁ በኋላ በሸዋ፣ በጎጃም ብሎም እስከ ጋሞ ጎፋ ብርብር ማርያም ድረስ ወንጌል ሰባክያን እየተላኩ ወንጌልን አስተምረዋል፡፡
የታሪክ ተመራማሪው ዶክተር ሥርግው ሐብለ ሥላሴ “The Establish event of the Ethiopian church” በሚል ርእስ ባቀረቡት የጥናት ወረቀታቸው ላይ፤ ከላይ በአቡነ ጎርጎርዮስ የተገለጠውን ዘመነ ፍሬምናጦስ በኢትዮጵያ ክርስትና ውስጥ ያለውን ታሪካዊ ቦታ ሲያብራሩ፤ “የክርስትና ሃይማኖት እንደመንግሥታዊ ሃይማኖት መተዋወቁ በኢትዮጵያ ታሪክ ወሳኝ ነጥብ መሆኑን ያሳያል” ካሉ በኋላ “ክርስትና በሀገሪቱ የሚያካትተው ንጹሕ ሃይማኖታዊ ክስተቶችን ብቻ አይደለም፡፡ በሁሉም ሀገራዊ ኑሮ ላይ ዘርፈ ብዙ ሚና አለው፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቱ ሃይማኖታዊ ብቻ ሳትሆን ለበርካታ ዘመናት የአገሪቱ ሕዝብ የባህል፣ የፖለቲካና ማኅበራዊ ኑሮ ግምጃ ቤት መሆኗን ያሳያል” ይላሉ፡፡
ዘመነ ቅዱስ ፍሬምናጦስ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲየን መንበረ ጵጵስና ታሪክ ውስጥ ያለውን ሀገራዊና ዓለም አቀፋዊ ፋይዳ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ “የኢትዮጵያ ኦርቶዶክሪስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ” በሚለው መጽሐፋቸው “ከርሱ /ከቅዱስ ፍሬምናጦስ/ ጀምሮ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በመንበረ ጵጵስና ከሌሎች ጥንታውያን አብያተ ክርስቲያናት ጋር እኩል ሆነች፡፡” ብለው ሲገልጹ “የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ትናንትናና ዛሬ” በሚል ርእስ በቤተ ክርስቲያኒቱ የሊቃውንት ጉባኤ የተዘጋጀው መጽሐፍ ደግሞ “…. ቅዱስ ፍሬምናጦስ በዚህ ሁሉ ሥራው ከሣቴ ብርሃን ሰላማ የሚል ቅጽል ተሰጠው፡፡ ከእርሱ ጀምሮ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በመንበረ ጵጵስና ደረጃ ታወቀች” በማለት ነው፡፡

የኢትዮጵያን ዕሥራ ምዕት ምክንያት በማድረግ በቤተ ክርስቲያኒቱ ሊቃውንት “የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስትያን ታሪክ ከልደተ ክርስቶስ እስከ 2000 ዓ.ም” በሚል ርእስ የተዘጋጀው መድበል ይህንኑ ሐሳብ ሲያጠናክር፤ “ቅዱስ አባ ሰላማ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ መንበረ ጵጵስናውን አክሱም ላይ አድርጎ በሀገራችን የወንጌልን ብርሃን በሰፊው ስለገለጠ ከሣቴ ብርሃን ተባለ” ይልና “በዚሁ በአራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በዓለም አቀፍ ደረጃ የታወቀች ብሔራዊት ቤተ ክርስቲያን ለመሆን መብቃቷን ታሪክ ያስረዳል” ይላል፡፡

የኢትዮጵያን ታሪክ ስንመለከት የአንድም ሐዋርያ ደም ሳታፈስ፣ የአንድም ሰማዕት አጥንት ሳትከሰክስ ኦርቶዶክሳዊት ሃይማኖትን የተቀበለች ሀገር ነች፡፡ ይኼ እንዲሆን ደግሞ ከሕዝባችን ጨዋነት ባሻገር የመንግሥት እና ቤተ ክህነት ግንኙነትም ወሳኝ ታሪካዊ አጋጣሚም ነበር፡፡ ቀደም ብሎ የንግሥተ አዜብ ወደ ሰሎሞን መሔድና የቀዳማዊ ምኒልክ ከሰሎሞን መወለድ ለሥርዓተ ጽዮን አገባብና ለሕገ ኦሪት አመጣጥ ምክንያት ሆነ፡፡ እንዲሁም ደግሞ በሕንደኬ ንግሥት ጊዜ የበጅሮንዷ ወደ ኢሩሳሌም መሔድና ከሐዋርያው ፊልጶስ ጋራ ተገናኝቶ የወንጌልን ዜና ጽድቅ ለማምጣት መሪ ሆነ፡፡ ቅዱስ ፍሬምናጦስ በኢትዮጵያ ቤተ ክህነትና ቤተ መንግሥት አማካኝነት ተመርጦ ወደ እስክንድርያ ሔዶ ጵጵስና ተሹሞ መጠቶ እስካሁን ሲያያዝ የመጣውን የወንጌል መክሊት በብዙ ሚሊዮን ለሚቆጠሩ ምእመናን አተረፈ፡፡ ይኼ ደግሞ ሌላኛው ቤተ ክርስቲያናችን የተገነባችበት የታሪክ ገጽታችን ነው፡፡
የዚህ ዓይነቱ ታሪካዊ ትስስር በወቅቱ ከነበረው ዓለም አቀፋዊ ነባራዊ ሁኔታ አንጻር ቤተ ክርስቲያኒቱ የነበረችበትን ታሪክዊ ቦታ ዶክተር ሥርግው ሐብለ ሥላሴ “The Establishment of the Ethiopian church”  በሚለው ጥናታቸው ሲተነትኑ “የክርስትና ሃይማኖት እንደ መንግሥት ሃይማኖት በኢትዮጵያ መግባቱ በተደራጀ በሌላ ሀገር የስብከት ውጤት ሳይሆን የነገሠታቱ /አማኝነት/ ነው” ካሉ በኋላ “ክርስትና በኢትዮጵያ የተዛመተው እንደ ግሪክ ሮማውያን ዓለም ዓይነት የክርስትና ተዛምቶ መንገድ አይደለም፡፡ ክርስትና በእነዚህ ሀገሮች ለሦስት ምእት ዓመታት በታችኛው የኅብረተሰብ ክፍል ቢታቀብም ወዲያው የገዢው መደብ ተቃውሞታል፡፡ በእርግጥ በአራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን መጀመሪያዎች በጣም ጥቂት የሚሆኑ የነገሥታት ቤተሰቦች የክርስትና ሃይማኖትን መቀበል ቢጀምሩም በኢትዮጵያ ግን መቀበሉ ከምር ነበር፡፡ ክርስትናው በመጀመሪያ በቤተ መንግሥቱ ገባ፣ ከዚያ ቀስ በቀስ ወደመላው ሕዝብ ተዛመተ፡፡ በሮማ ግዛት ዐፄ ሕዝቡን በክርስትና ሃይማኖት ለማሳመን ሐዋርያትና የኋላ ዘመን አባቶች ሲሳተፉ፣ በኢትዮጵያ ክርስትና በፈቃደኝነት ገባ” ይላሉ፡፡ ይህ ማለት ሐዋርያዊ፣ አገልግሎት አልነበረም ለማለት እንዳልሆነ ልብ ይሏል፡፡
ዶክተር ሥርግው ሐብለ ሥላሴ ትንታኔያቸውን በመቀጠል፤ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን እንደ መንግሥት ሃይማኖት ከርስትናን ስትቀበል ስለነበረው ወቅታዊ ዓለም አቀፍ ሁኔታም ሲያብራሩ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓቷ እየተጠናከረ በምትቋቋምበት ወቅት የአርዮስ ክህደት ጫፍ ላይ ደርሶ ነበር፡፡ ቅዱስ ፍሬምናጦስ በቅዱስ አትናቴዎስ በሚመራው የእስክንድርያ መንበር ሥር ሆኖ በኒቅያ ጉባኤ አርዮስን ከሚቃወሙ የኦርቶዶክሳውያኑ ወገን ነበር፡፡ ይህም የሆነው የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በብሔራዊነት ከመመሥረቷ በፊት ነው፡፡ ነገር ግን የጉባኤው ውሳኔ አስገዳጅ ባይሆንም ኢትዮጵያ ከአትናቴዎስ እና ከኒቅያ እምነት ነች ካሉ በኋላ በወቅቱ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ከአርዮሳውያን የገጠማትንም ፈተና ሲገልጹም፤ “የታላቁ ቆስጠንጢኖስ ልጅ ቆንስጣ ወደ አርዮስ ምንፍቅና ለማምጣት ጥረት አድርጎ ነበር፡፡ በዚህ ምክንያትም ለኢዛና እና ሳይዛና ቅዱስ ፍሬምናጦስን ወደ እስክንድርያ እንዲልከውና የእርሱም ሃይማኖት እንዲፈተሽ ደብዳቤ በመላክ ጠይቆ ነበር፡፡ ዓላማውም የኦርቶዶክሳዊነትን ዓለም ተቀፋዊ ተቀባይነት ማረጋገጥ ነበር፡፡ በዚህ አንጻር በኢትዮጵያ ላይ ያደረጉት ተልእኮ ሳይሳካ ቀረ፡፡ ቅዱስ ፍሬምናጣስም ከአትናቴዎስ የተማረውን ትምህርት እያስተማረ በአክሱም ቀረ፡፡” በማለት ነው፡፡ ይኼ እንግዲህ አንዱ የታሪኳ አካል ነው፡፡

ዘመነ ተሰዓቱ ቅዱሳን

ዶክተር ሥርግው ሐብለ ሥላሴ “The Expansion and consolidation of Christianity” በሚል ርእስ በአሰፈሩት መጣጥፋቸው ደግሞ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የሐዋርያነት አገልግሎት ምን እንደሚመስል ያስቃኙናልና፡፡ “እንደ ኢትዮጵያ ጳጳሳት ታሪካዊ ቅደም ተከተል ዝርዝር ከሆነ ቅዲስ ፍሬምናጦስ የተተካው በአቡነ ሚናስ ነው፡፡ መካነ ልደቱም ከግብጽ ነው፡፡ ከዚህ ጊዜ ጀምሮ ለአንድ ሺሕ ስድስት መቶ ዓመታት የግብጻውያን ልዩ የሆነው አገዛዝ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ላይ ተጫነ፡፡ በዚህ ዘመን በግብጻውያን ዘንድ ሁሉ ኢትዮጵያውያን ለሢመተ ጵጵስና ብቁዎች ተደርገው አይወሰዱም፡፡ ሚናስ ስለራሱ ሐዋርያዊ አገልግሎት ጥቂት የሥነ ጽሑፍ መረጃ ቢተውም በሐዋርያዊ አገልግሎት በከፍተኛ አስተዋጽኦነቱ የሚጠቀሰው የዘጠኙ ቅዱሳን አገልግሎት ነው” ይላሉ ዶክተር ሥርግው ሐብለ ሥላሴ ከላይ በጠቀስነው ጽሑፋቸው፡፡
እኚህ የታሪክ ምሁር “The Religious Life in Ethiopia” በተባለው የጥናት ወረቀታቸው ደግሞ እነዚህ ቅዱሳን ሐዋርያነትን መሠረት በአደረገው አስተዳደራዊና ማኅበራዊ አገልግሎት ቤተ ክርስቲያኒቱን በየትኛው የታሪክ ምዕራፍ ላይ እንደአስቀመጡ ሲገልጹ “በዘጠኙ ቅዱሳን ቤተ ጣዖትንና የቆዩ ማእከለ ሁሉን አምላኪዎች /Pagan centers/ ወደ ክርስትና ማእከልነት ለወጡ፡፡ በዚህ ሒደት ከሕዝቡ ምንም ተቃውሞ አልገጠማቸውም፤ አንድም ቅዱስ አልተሰዋም” ይላሉ፡፡
ይህ ሒደት በሀገሪቱ የክርስትና ታሪክ ውስጥ አንዱ አስደሳች ክስተት ነው፡፡ በዘጠኙ ቅዱሳን መምጣት ምክንያት የተስፋፋው የክርስትናው ሃይማኖት ብቻ ሳይሆን የአገሪቱም ባህል ክርስቲያናዊ እንዲሆን ተደርጓል፡፡ ይህም የጥንቱ የክርስትና አገባብ ጠባይ ነው፡፡ የሚሉት ዶክተር ሥግግው ሐብለ ሥላሴ “ይኼ ሃይማኖታዊ ክስተት ብቻ ሳይሆን የማኅበራዊ አገልግሎት፣ የኅብረተሰቡ የማኅበራዊ ኑሮ አካል ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን የእግዚአብሔር ማምለኪያ ሥፍራ ብቻ ሳትሆን የተለያዩ ማኅበራዊ ችግሮች መፍቻ ቦታ መሆኗም በእነዚህ ቅዱሳን ተግባር ተረጋግጧል፡፡” ይላሉ፡፡ ከዚያም በመቀጠል “በጥቅሉ እነዚህ ቅዱሳን ቤተ ክርስቲያኒቱ ወይም ክርስትና እንደ ሃይማኖት ክስተት ሃይማኖታዊ ተቋም እና በማኅበረሰቡ ውስጥ ደግሞ ማኅበራዊ አገልግሎት ሰጪ እንድትሆን አድርገዋታል” ይላሉ፡፡
ብፁዕ አበኑ ጎርጎርዮስ “የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርሰቲያን ታሪክ” በተባለው መጽሐፋቸው እነዚህ ቅዱሳን ኦርቶዶክሳዊት ሃይማኖታችንን እንዴት እንደ አጸኑም ሲገልጹ “… በእነዚህ ዘጠኙ ቅዱሳን የጸናችልን ሃይማኖታችን ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ትባላለች፡፡” በማለት ነው፡፡ እነዚህ ቅዱሳን ቤተ ክርስቲያኒቱን ያጸኑበትን የአገልግሎት ትሩፋታቸውን “የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ትናንትናና ዛሬ” በሚል ርእስ የተዘጋጀው መጽሐፍ ሲዘረዝር “ሥርዓተ ምንኩስናን፣ ገዳማዊ ሕይወትንና ምናኔን ማስተማር፣ ገዳማትን በየቦታው ማቋቋም፣ በቅዱስ ፍሬምናጦስ ጊዜ ያልተተረጎሙ መጻሕፍትን መተርጎም፤ በከሣቴ ብርሃን ሰላማ ጊዜ የተቋቋመችውን ቤተ ክርስቲያን ማጠናከር” በማለት ነው፡፡
ዲያቆን ዳንኤል ክብረት “የሐዋርያት ሥራ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን አጭር መግቢያ” በሚል ርእስ በጻፈው መጣጥፉ እንደገለጸው፣ ዘጠኙ ቅዱሳን በትግራይና አካባቢዋ ወንጌልን በማስፋፋት ቅዱስት መጻሕፍትን በመተርጎምና ገዳማትን በማስፋፋት ለሐዋርያነት ተልእኮ ታላቅ አስተዋጽኦ አድርገዋል፡፡ በዚህም የመጀመሪያው ዘመን በኤርትራ፣ ትግራይ፣ ወሎ፣ ጎንደር ጎጃምና ሸዋ ሀገረ ስብከት ወንጌልን ማስፋፋት ተችሏል፡፡ በትግራይ የተሰዐቱ ቅዱሳን ገዳማት፣ በወሎ የተድባበ ማርያም ደብር፣ በሸዋ በጥንቱ ዞረሬ በዛሬው ደረሳ ብርቴ ጥረት የተደረገው በዚህ ዘመን ነው፡፡
ከተግባራቸው ተንሥተው የዘጠኙ ቅዱሳን ወደ ኢትዮጵያ መምጣት በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ያለውን አንድምታ ዶክተር ሥርግው “The Expansion and consolidation of Christianity” በተባለው የጥናት መጣጥፋቸው ሲጠቅሱ “…. የዘጠኙ ቅዱሳን ወደ ኢትዮጵያ መምጣት በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ሃይማኖታዊ ሕይወት እና በሀገሪቱ የባህል ዕድገት ውስጥ አዲስ ምዕራፍ የከፈተ ነው” በማለት ነው፡፡ “የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ ከልደተ ክርስቶስ እስከ 2000 ዓ.ም” የተባለውም መድበል ከላይ የጠቀስነው የዶክተር ሥርግውን ሐሳብ በማጠናከር እንዲህ ይላል፡፡
“ከዘጠኙ ቅዱሳን መምጣት በኋላ የአክሱም ቤተ መንግሥትና መላው የኢትዮጵያ ግዛት በክርስትና ሃይማኖት ትምህርትና ስብከት ተደርሶ ነበር፡፡ ተሰዐቱ ቅዱሳን ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ጥንካሬ ከፍተኛ ተልእኮን ፈጽመው ስለዐረፉ ቤተ ክርስቲያናችን ቅዱሳን ብላ ታከብራቸዋለች”
በዚሁ መጽሐፍ ብፁዕ አቡነ ገሪማ “የኢትዮጵያ ኦርቶዶክሪስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አስተዳደርና መንግሥት በየዘመናቱ” በሚል ርእስ ባቀረቡት ጽሑፍ ተሰዓቱ ቅዱሳን በአመራራቸው በሕዝበ ክርስቲያኑ እንደሚወደዱ ገልጸዋል፡፡
እንግዲህ ከነዚህ የመጀመሪያዎቹ የክርስትና ዘመናት ክንዋኔዎች ተነሥተን ቤተ ክርስቲያኒቱ በወቅቱ ተልእኮዋን ለመወጣት የሚያስችላት የወቅቱ አደረጃጀት እንደነበራት መደምደም ይቻላል፡፡ ይኼንም አደረጃጀት ዶክተር ሥርግው ከላይ በጠቀስነው የጥናት ጽሑፋቸው ላይ የጠቀሱት “ከክርስትና መስፋፋት በኋላ በኢትዮጵያ ውስጥ ቢያንስ አራት አህጉረ ስብከት ነበር፡፡ እያንዳንዱ የሚመራው በጳጳስ ነበር፡፡ የእነዚህም ርእስ የአክሱም ሊቀ ጳጳስ እንደሆነ ግልጽ ነው፡፡ አስቀድመን እንደገለነጽነው ሁሉም ጳጳሳት መካነ ልደታቸው ግብጽ ወይም ግብጻውያን ናቸው፡፡ በዶግማም ሆነ በአስተዳደር ከግብጹ ፓትርያርክ ጋራ የጠበቀ ግንኙነት አላቸው፡፡ በኢትዮጵያ ላይ የሚያስፈጽሙት የግብጽን ፍላጎት ነበር፡፡ ይህም በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ውስጥ ልዩ ክስተት ነው” በማለት ነው፡፡
ከዚህም በተጨማሪ በአራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን የቤተ ክርስቲያኒቱ አስተዳደር የነበረበት ሁኔታ ብፁዕ አቡነ ገሪማ ከላይ በጠቀስነው መጽሐፍና ርእሰ ጉዳይ ላይ “አራተኛው መቶ ዓመት በቅዱሳን ነገሥተ ኢትዮጵያ አብርሃ ወአጽብሐ ዘመን መንግሥት፤ በቅዱስ ፍሬምናጦስ ዘመን ክህነት ስብከተ ወንጌል የተስፋፋበት የቤተ ክርስቲያኒቱ አስተዳደር አምሮ፣ ሰምሮ፣ የታየበት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክረስቲያን ብሔራዊት የሆነችበት ጊዜ ነበር” ይላሉ፡፡
ከዚህም ጋር አያይዘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከአራተኛው መቶ ዓመት እስከ ዐሥራ አምስተኛው መቶ ዓመት እስከ ዐሥራ አምስተኛው መቶ ዓመት በነበሩት በዘመናት በመካከሉ በየጊዜው ችግር ቢያጋጥምም ሁለንተናዊ የሆነ አርኪ የቤተ ክርስቲያን ታሪካዊ አስተዳደር የተፈጸመበት ዘመን መሆኑን አበክረው ይገልጻሉ፡፡
እንግዲህ ቤተ ክርስቲያን በፊት በኢትዮጵያው ጃንደረባ የተሰበከችልን በቅዱስ ፍሬምናጦስ እና በዘጠኙ ቅዱሳን የጸናችልን ነች፡፡ ከዚያም በኋላ የእስልምና መነሳት፣ የዮዲት ጉዲት ጥፋትና የግራኝ አህመድ ውድመት በቤተ ክርስቲያኒቱ በየዘመኑ ቢፈራረቁም በርካታ ወርቃማ ሥራዎች ተሠርተዋል፡፡ ከአለው ነባራዊ ሁኔታ ከዚህ በላይ መሔድ አንችልም፡፡ የት ነበርን የሚለውን ለማሳየት የክርስትና የመጀመሪያዎቹን ዘመናት አይተናል፡፡ ቦታ ኖሮን እያንዳንዱን ዘመን ብናይ አሁን ከአለንበት ጋራ ስናነጻድር እጅግ ያስቆጭ ነበር፡፡ ይሁንና አሁን ያለውን ነባራዊ ሁኔታ ለማየት ያነሳናቸው ማሳያዎች በቂ ናቸው፡፡

ቤተ ክርስቲያኒቱ አሁን ያለችበት ሁኔታ
እንግዲህ ቤተ ክርስቲያኒቱ በየዘመናቱ የተለያዩ ፈተናዎች ቢገጥሟትም አስቀድመን እንደተመለከትነው ተልእኮዋን በአግባቡና ሥርዓታዊ በሆነ መልኩ ትወጣ ነበር፡፡ በዚህ መልኩም ከእኛ ዘመን ደርሳለች፡፡ ይሁንና አሁን ያለችበት ነባራዊ ሁኔታ ከጊዜ ወደጊዜ እየተወሳሰበ ከመምጣቱ የተነሣ ተልእኮዋ ላይ አደጋዎች ተጋርጠዋል፡፡ እነዚህን በሦስት ከፍለን እናቀርባለን፡፡
ሀ. አስተምህሯዊ ቅሰጣ
ቤተ ክርስቲያን የተመሠረተችው ወልድ ዋሕድ በሚለው መሠረተ እምነት እና ነቢያት፣ ሐዋርያት ስለ ወልድ ዋሕድ መሠረተ እምነት በአስተማሩት ትምህርት ላይ ነው፡፡ እነዚህን የመሠረተ እምነት ትምህርቶች ከምእመናን ልቡና የማራቅና ከቤተ ክርስቲያኒቱ ዐውደ ምሕረት የማስወገድ ሥራ በከፍተኛ ሁኔታ የእርሷ ነን በሚሉ በተግባራቸው ግን ባልሆኑት እየተሠራ ነው፡፡ ይኼም ሥራ እየተሠራ ያለው በተሐድሶ ኑፋቄ አንቀንቃኞች፣ ሰባክያንና የስሕተት ትምህርት ባዘሉ መጻሕፍት ጸሐፊያን ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያኒቱን ሥርዓተ አምልኮ፣ ትውፊትና ታሪክ የመከለሱና የመበረዙ ሥራ በነዚሁ አካላት ተጧጡፏል፡፡ በአንጻሩ ደግሞ ቤተ ክርስቲያኒቱ ይህን አደጋ በአግባቡ የተረዳና ተገቢውን የመፈትሔ አቅጣጫ የሚያስቀምጥ የስብከተ ወንጌል ዕቅድና ግብ የላትም፡፡ ለዚሁ ተግባር ማስፈጸሚያ ተገቢ አደረጃጀት፣ የሰው ኃይልና በጀት አትመድብም፡፡ ይኼ ደግሞ ችግሩ እጅግ አሳሳቢና የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ ተልእኮ በማሳካት ረገድ መጪውን ዘመን ጨለማ ያደርገዋል፡፡ ለዚህ እንደማሳያ የሚጠቀሰው በ1999-2000 ዓ.ም በተካሔደው የሕዝብና ቤቶች ቆጠራ ውጤት በግልጽ የታየው እውነታ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ምእመናንን ቁጥር ከ50.6 በመቶ ወደ 43.5 በመቶ ወርዷል፡፡  በከተማ ቤተ ክርስቲያናችን ያላት የምእመናን ድርሻ እየቀነሰ መጥቶ ወደ 59.1 በመቶ ሲሆን በገጠር ደግሞ 40.5 በመቶ ነው፡፡ በአጠቃላይ ቤተ ክርስቲያኒቱ በሀገር አቀፍ ደረጃ ያለው ድርሻ ቁልቁል እየወረደ መሆኑን ያሳያል፡፡ በሀገር አቀፍ ደረጃ የ7.1 በመቶ መቀነስ አሳይቷል፡፡ ይኼ ሁኔታ በዚህ መልኩ ከቀጠለ የቤተ ክርስቲያን ህልውና አደጋ ላይ መሆኑን ለመጠቆም ነቢይ መሆን አያስፈልግም፡፡ በዚህ ሒደት ውስጥ ደግሞ የእርሷን እንጀራ እየበሉ በሌላው ደጅ የሚጠኑ ሰዎቿ ድርሻውን ይወስዳሉ፡፡
ለ. አስተዳደራዊ ችግር
የቤተ ክርስቲያኒቱ ዋነኛ ተልእኮዎች የሆኑት ማጥመቅ፣ ማጽናትና መከታተል መሆኑ እየታወቀ ይህን ተልእኮ ማሳካት የሚያስችል የተጠናከረ አስተዳደራዊ አደረጃጀትና የሰው ኃይል የለም፡፡ የቤተ ክርስቲያኒቱ አስተዳደራዊ አደርጃጀትና አወቃቀር ወቅቱ ከሚጠይቀው፣ አሁን ካሉት ሥራዎች ስፋትና ከልማትና ማኅበራዊ እንቅስቅሴዎች ጋር አብሮ የሚጓዝ አይደለም፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን ወቅቱን በመዋጀት ከጊዜው ጋራ እንዳትራመድ አድርጓታል፡፡
ቅዱስ ሲኖዶስ የቤተ ክርስቲያኒቱን ፖሊሲ በማውጣትና ስትራቴጀ በመንደፍ የመምራት ሓላፊነቱንና አደራውን በብቃት ለመወጣት በሚያስችል ሁኔታ አልተደራጀም፡፡ የሚወስናቸውን ውሳኔዎች አፈጻጸም የሚከታተልበትና የሚገመግምበት መከታተያና መገምገማያ እንዲሁም የአሠራር ሥርዓት የለውም፡፡
እንደሚታወቀው የአሠራር መዋቅር ተቋማዊ ግብን የማስፈጸም ሥርዓት እና ብቃት እንዲኖረው ተደርጎ ይዘጋጃል፡፡ በቤተ ክርስቲያኒቱ መዋቅራዊ የአሠራር ሥርዓትን ጠብቆ ጉዳይን በወቅቱ ማስፈጸምም ሆነ መፈጸም አስቸጋሪ ነው፡፡ በየደረጃው የሚገኙ የቤተ ክህነቱ አሠራር መዋቅሮች የቅዱስ ሲኖዶስን ውሳኔዎች የማስፈጸምም ሆነ የመፈጸም ግዴታ ቢኖርባቸውም መዋቅራዊ የአሠራር ሥርዓቱ ልል ከመሆኑ የተነሣ ይህ ሲሆን አይታይም፡፡ የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔን ከአስፈለገ አንድ የአጥቢያ አስተዳዳሪ የሚጥስበት፣ የጠቅላይ ሥራ አስኪያጅን የሥራ መመሪያ አንድ የመምሪያ ሓላፊ ተገቢና ምክንያታዊ ባልሆነ መንገድ የማይቀበልበት እና የማያስፈጽምበት ሁኔታ አለ፡፡
በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ የሚታየው የአስተዳደራዊ አሠራር ክፍተት እንዲህ መሆኑ የራሳቸውን አጀንዳ ለማስፈጸም በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ ለሚንቀሳቀሱ አካላት ምቹ መስፈንጠሪያ ሆኖላቸዋል፡፡ በየትኛውም አግባብ በየትኛውም የአሠራር መዋቅር የሚፈልጉትን ያስወስናሉ፤ ያልፈለጉትን ውሳኔ ያሽራሉ፡፡
ገዳማቱና የአብነት ትምህርት ቤቶቹም የሚገኙበት አስከፊ ገጽታም የአስተዳደራዊ ችግሩ ነጸብራቅ ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያኒቱ በሚፈጠሩ የተለያዩ አስተዳደራዊ ችግሮች የተነሣ ገዳማቱ ያላቸውን ጥቂት ገቢ፣ መሬት፣ የሰው ኃይልና ሌሎች ሀብቶችን እንዳይጠቀሙ አድርጓቸዋል፡፡ ይህም ገዳማቱን ወደ ቁሪት ገዳምነት እንዲቀየሩ ምክንያት ሆኗል፡፡ በገዳማት ሊኖር ይችል የነበረውንም የልማት ተሳትፎ በእጅጉ ጎድቶታል፡፡ የአብነት ትምህርት ቤቶች ለደቀ መዛሙርቱ እና ለመምህራኑ ምግብና መጠለያ ማግኘት ተስኗቸው ትምህርት ቤቶቹ እንዲዘጉና እንዳይስፋፉ የሆነውም የአስተዳደራዊው ችግር ውጤት ነው፡፡ በዚህ መልኩ በየገዳማቱና የአብነት ትምህርት ቤቶቹ የሚታየው ችግር በዚህ ሁኔታ ከቀጠለ የነገይቱን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የሚተካ ትውልድ ማግኘትን ከባድ ያደርገዋል፡፡
የአስተዳደሪዊው ችግር ውጤት /Effect/ ያረፈው በገዳማቱና በአብነት ትምህርት ቤቶቹ ብቻ ሳይሆን በካህናቱም ኑሮ ላይ ነው፡፡ ካህናት የሚያገኙት ደመወዝ አሁን ካለው የገበያ ሁኔታ አንጻር ቤተሰቦቻቸውን ለማስተዳደር በቂ አይደለም፡፡ ተምረው ነገ ሀገርንና ቤተ ክርስቲያንን ያገለግላሉ፣ ኑሯችንን ያሻሽላሉ፤ ጧሪ ቀባሪያችን ይሆኑናል የሚሏቸውን ልጆቻቸውን ዘመናዊ ትምህርት ማስተማር እንዳይችሉ ተፅዕኖ አድርጎባቸዋል፡፡ ከዚህ ሲብስም “እኔ በየአብነት ት/ ቤቱ ብዙ ደክሜ የቤተ ክርስቲያኒቱን ትምህርት ተምሬ ምን አገኘሁ” በሚል ልጆቻቸውን ከቤተ ክርስቲያኒቱ ትምህርት እንዲያርቁ አድርጓቸዋል፡፡
የቤተ ክርስቲያኒቱን መንፈሳዊና ቁሳዊ ሀብት /የሰው ኃይል፣ ገንዘብ፣ ንብረት/ አመራር ሠራተኞችን፣ ገንዘብንና ንብረትን በአግባቡና ዘመኑ በሚጠይቀው የአሠራር ዘይቤ በማቀናጀት የቤተ ክረስቲያኒቱ ዋነኛ ተልእኮ ማስፈጸሚያ የሆነውን ሐዋርያዊ አገልግሎት ለማስፋፋትና ማኅበራዊና ምጣኔ ሀብታዊ አስተዋጽኦ ለማድረግ የሚያስችል ዕውቀትና ልምድ ያለው የሰው ኃይል እና አስተዳደር ሥርዓት የላትም፡፡ ይህ ደግሞ የመጪው ዘመን ቀጣይ አገልግሎቷን በሚፈለገውና ወቅቱ በሚጠይቀው መጠን ውጤታማ አያደርገውም፡፡
በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/    ቤትና በየአህጉረ ስብከት የሓላፊዎች ምደባ የትምህርት ዝግጅትን ሙያና ችሎታን ወይም ብቃትን መሠረት ያደረገ አይደለም፡፡ ይኼ ደግሞ በቤተ ክርስቲያኒቱ ከፍተኛ የሆነ የአመራር እና አስተዳደር ችግር የሀብት ብክነትና ዝርፊያ፣ ውዝግብና የመልካም አስተዳደር ዕጦትን አንሰራፍቷል፡፡ ይህ ሁኔታ በዚህ መልኩ የሚቀጥል ከሆነ ቤተ ክርስቲያኒቱ ለቤተ ክረስቲያኒቱ ተልእኮ ግድ የሌላቸው ሰዎች መጠራቀሚያ ትሆናለች፡፡ ምእመኑም ባለው አመራር ላይ እምነቱን እያጣ ሲሔድ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ማበርከት የሚገባውን በጎ አስተዋጽኦ ከማበርከት ሊታቀብ ይችላል፡፡
ሐ. ዘመናዊ የፋይናንስ አስተዳደር አለመኖር
ቤተ ክርስቲያኒቱ  ተልእኮዋን መፈጸም የሚያስችላት በማእከላዊነት የሚተዳደር ዘመናዊ የፋይናንስ አያያዝና አጠቃቀም ሥርዓት የላትም፡፡ አብያተ ክርስቲያናት ከምፅዋት ከሚያገኙት ገንዘብ ባሻገር የተለያዩ የገቢ ማስገኛ ሕንፃዎች እየገነቡ የተለያዩ የልማት ሥራዎችን ለመሥራት ጥረት ቢያደርጉም የፋይናንስ አያያዛቸውና አጠቃቀማቸው ለብክነትና ምዝበራ የተጋለጠ ነው፡፡ በቤተ ክርስሪቲያኒቱ ውስጥ ጠንካራ የፋይናንስና የኦዲት ሥርዓት እንዲሁም ሓላፊነትና ተጠያቂነት ያለበት በዕቅድና ሪፖርት የታገዘ የአሠራር ሥርዓት የለም፡፡ በዚህ ምክንያት ለልማት ሊውል የሚችለው የቤተ ክርስቲያኒቱ አንጡራ ሀብት ሊባክን ከመቻሉም በላይ ጠንካራ ልማት ሊመጣ አልቻለም፡፡
እንዲህ ዓይነቱ የፋይናንስ አያያዟና አጠቃቀሟ የቤተ ክርስቲያኒቱን መሠረታዊ ተልእኮ ከማደናቀፉም በላይ የራሷን አገልጋዮች በአመዛኙ ከችግር ማሳቀቅ ያልቻለበት ደረጃ ላይ ይገኛል፡፡ ይህም ቤተ ክርስቲያኒቱ በሐዋርያዊ ተልእኮዋ አፈጻጸሟ እንድትደክም ከማድረጉም ባሻገር የሙስናው ጽንፍ ቤተ ክርስቲያኒቱን በምእመናን ዘንድ ያላትን አመኔታና ከበሬታ እያሳጣት ነው፡፡
በአጠቃላይ በቤተ ክርስቲያኒቱ ማእከላዊ የሆነ የፋይናንስ አስተዳደር ባለመኖሩ አገልጋዮቿ ገጠሩን እየተው ገቢ ይገኝባቸዋል ወደሚሏቸው ከተሞች እንዲጎርፉ አድርጓቸዋል፡፡ ይህ ደግሞ በገጠር የሚገኙትን ብዙ አብያተ ክርስቲያናትን ያለ አገልጋይ በማስቀረቱ እንዲዘጉ ሆነዋል፡፡ እዚህ ላይ ሆነን የነገይቱን የገጠሪቱን ቤተ ክርስቲያን ስናስብ ስጋት ላይ ይጥለናል፡፡
ቤተ ክርስቲያኒቱ በስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ እንዲሁም በማኅበራዊ አገልግሎትና ልማታዊ ሥራዎች ሊደግፏት የሚችሉት የአገልግሎት ሰጪ ተቋማት በምዝበራና ብኩንነት እየተዳከሙና የሚጠበቅባቸውን ያህል ፍሬያማ ሊሆኑ አልቻሉም፡፡ እንዲህ ዓይነቱ ችግር ሥር እየሰደደና እየጸና ከሔደ ቤተ ክርስቲያኒቱ ለማትወጣው አዘቅት ሊዳርጋት ይተላል፡፡ የጥቂት ግለሰቦች ፈላጭ ቆራጭነት እየጨመረ መዋቅራዊ ውሳኔዎችና አፈጻጸሞች እየከሰሙ ከሔዱ የቤተ ክርስቲያኒቱ የወደፊት ዕጣ ፋንታ በግለሰቦች እጅ እንዲሆን ሊያደርግ ይችላል፡፡ አሁን እየታየ ያለውም በአመዛኙ የዚሁ ተመሳሳይ ነው፡፡
የመፍትሔ አቅጣጫ ጥቁምታ
በአደጋ ቁልቁለት ላይ ያለውን የቤተ ክርስቲያኒቱን አስተምህሯዊ ቅሰጣ-አስተዳደራዊ ፋይናንሳዊ ችግሮች ለመቅረፍ ቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጧን በአስቸኳይ የምትፈትሽበት መፍትሔና አፋጣኝ የአሠራር ሥርዓት መዘርጋት አለባት፡፡
ቅዱስ ሲኖዶስ፤ ቤተ ክርስቲያናችን ዋናና ተቀዳሚ ዓላማዋ የሆነውን ሐዋርያዊ አገልግሎት በማስፋፋት፣ የምእመናንን ክርስቲያናዊ ሕይወት የማጽናትና የማጠናከር እንዲሁም ያላመኑትን በማስተማርና በማሳመን ተልእኮዋን ማሳካት የሚያስችላትን ተገቢውን አደረጃጀት፣ የሰው ኃይልና በጀት ሥርዓትም እንዲኖር በማድረግ ረገድ ቀዳሚ ሓላፊነት እንዳለበት ይተወቃል፡፡
ከዚህም በተጨማሪ ከውስጥ ሆነው የቤተ ክርስቲያኒቱን ተልእኮ በማደናቀፍ ከሌሎች የተለየ ዓላማ ካላቸው ጋር ሽርክና መፍጠር ምእመናንን ከበረታቸው እያስኮበለሉ ባሉት ላይም በቀኖና ቤተ ክርስቲያን መሠረት እርምጃ የሚወስድበትን አቅጣጫ ቅዱስ ሲኖዶስ ማስቀመጥ አለበት፡፡
ቤተ ክርስቲያኒቱ በአስቸኳይ ውስጧን በመፈተሽ ጊዜ እና መስክ ወለድ ለሆኑ መሠረታዊ ፈተናዎችና ችግሮች ዘለቄታ ያለው፣ ተጨባጭና ችግር ፈቺ መፍትሔ ማስቀመጥ አለባት፡፡ ከዚህ አንጻር የቤተ ክርስቲያኒቱ መዋቅራዊ አደረጃጀት መሠረታዊ ተልእኮዋን ለማስፈጸም፣ ቀልጣፋ አሠራርን፣ ግልጽ፣ ሓላፊነትና ተጠቃቂነት ሊያሰፍን በሚያስችል መልኩ አስተዳደራዊ የመዋቅር ማሻሻያ ማድረግ ይኖርበታል፡፡
ሙሉ ሥልጣንና ሓላፊነት ያለው በብፁዓን አበው የሚመራ፣ በሥሩ የተለያዩ ባለሙያ ምሁራንን ያካተተ የአማካሪ ቡድን የሚዋቀርበት አጠቃላይ የቤተ ክርስቲያኒቱን መዋቅራዊ እና አስተዳደራዊ ችግሮችን አጥንቶ የመፍትሔ ሐሳቦችን የሚጠቁም አካል እንዲቋቋም ማድረግ ይኖርበታል፡፡
ቅዱስ ሲኖዶስ የገዳማቱ ሥሪት ገቢያቸውን በራሳቸው እንዲቆጣጠሩ የሚያስችል በመሆኑና ወደ ሀገረ ስብከቶች ወይም ጠቅላይ ቤተ ክህነት የገቢ ፈሰስ እንዲያስገቡ የሚጠይቁ ባለመሆናቸው፤ ያለማንም ጣልቃ ገብነት የልማት ፕሮጀክቶችን በየገዳማቱ በተናጠል የሚሠራበትን አቅጣጫ ማስቀመጥ ለዚህም ሥራ ተስማሚ የሰው ኃይልና በጀት መመደብ፤ የቤተ ክርስቲያኒቱን ልማት የሚመራው አካል መንፈሳዊውን አገልግሎት ከሚመራና ከሚያከናውነው አካል ተለይቶ የልማት አስተደደሩ በቂ ዕውቀትና ልምድ ባለው የሰው ኃይል የሚመራበትን አስተዳደራዊና መዋቀራዊ ሁኔታዎች ማመቻቸት እና ማጠናከር ይኖርበታል፡፡
የቤተ ክርስቲያኒቱ የፋይናንስ አያያዝና አጠቃቀም ሥርዓት ዘመናዊና ወቅታዊ ድርብ የሒሳብ አያያዝን የተከተለ እንዲሁም የበጀት ሥርዐቱም በመደበኛና የካፒታል በጀት ተለይቶ በየዘመኑና በየሥራ ዘርፉ የበጀት ሥርዓት ተግባራዊ የሚሆንበትን፤ በየወቅቱ ሪፖርት እየቀረበበት ግምግማና ክትትል የሚደረግበትን አቅጣጫ ቅዱስ ሲኖዶስ ማስቀመጥ ይኖርበታል፡፡ ከዚህም ጋር አያይዞ ቤተ ክርስቲያኒቱ በማእከላዊነት የሚተዳደር የፋይናንስ አያያዝና አጠቃቀም ሥርዓት እንዲኖራት ማድረግ ወቅቱ የሚጠይቀው አሠራር በመሆኑ በተገቢው ሙያዊ ጥናት መሠረት ተግባራዊ የሚሆንበትን ሁኔታ ማመቻቸት ያስፈልጋል፡፡
የቤተ ክርስቲያኒቱ ላእላይ መዋቅር የሆነው ቅዱስ ሲኖዶስ ከላይ መፍትሔ ይሆናሉ በማለት የተጠቆሙትን ሐሳቦች እንዳላቸው ተጨባጭነትና ተግባራዊነት እንዲጠቀምባቸው አበክረን እንገልጻለን፡፡ ምክንያቱም አደጋው በዚሁ ከቀጠለ ቤተ ክርስቲያኒቱ ዐይናችን እያየ በአጭር ጊዜ ውስጥ በቀሳጮች ተውጣ፣ ታሪካዊና ወቅታዊ ልዕልናዋን አጥታና ሊኖራት የሚገባው ተደማጭነት ተሸርሽሮ አነስተኛ ቁጥር ተከታይ ያላት እንዳትሆን ስለምንሰጋ ነው፡፡ አሁን ያለው ነባራዊ እውነታም የሚያሳየው ይህንኑ ነውና፡፡
እንግዲህ ከላይ ለማሳየት እንደተሞከረው የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን አሁን ያለችበት ሁኔታ በመጀመሪያዎቹ የክርስትና ዘመናት ከነበረችበት ደረጃ ምን ያህል በችግር የተተበተበ እንደሆነ ብዙ የሚያከራክር አይመስለንም፡፡ ከዚህም በላይ ግን አሁን በምንንደረደርበት አቅጣጫ ከቀጠልን ከዚህም የከፋ ውስብስብና ዘመን ተሻጋሪ ችግሮችን ለመጪው ትውልድና ለነገይቷ ቤተ ክርስቲያን እንዳናስተላልፍ ያሰጋል፡፡ ይህም እንደትውልድ ከታሪክ፣ ከሕሊናና ከእግዚአብሔር ተጠያቂነት አያድነንም፡፡
ይህ ማለት ግን የተሻሉ ዕድሎች የሉም ማለት አይደለም፡፡ ከላይ ለመጠቆም እንደተሞከረው በቅዱስ ሲኖዶስ የመፍትሔ እርምጃዎች ቤተ ክርስቲያኒቱ ያላትን ሀብት በአግባቡ በመጠቀም ወደፊት ሊገጥሙን የሚችሉ አደጋዎችን በተሻለ ብቃት መሻገር እንችላለን፡፡ ይህ ሆኖ እንድናይ ደግሞ አሁን ያለንበትን አካላዊና ሥነ ልቡናዊ ድባብ በመሠረታዊነት ሊቀይሩ የሚያስችሉ ምሁራዊ እይታዎችንና ሒሶችን ማስፋትም ይጠበቅብናል፡፡
ውጤቱም የተጋረጡብንን መሠረታዊ ችግሮች መሻገር ብቻ ሳይሆን በቤተ ክርስቲያኒቱ ላእላይና ታህታይ የሥልጣን መዋቅር የሚቀመጡ የቤተ ክርስቲያኒቱ ልጆች በብቃታቸው፣ በሥነ ምግባራቸው፣ በመንፈሳዊ ተጋድሎ የታወቁ፣ ቤተ ክርሰቲያኒቱን ካለችበት አሰክፊ ችግር በዘላቂነት ለማውጣት ችሎታ፣ እልሁና ርእይ ያላቸው ይሆናሉ ብለን እናምናለን፡፡ አምላከ ቅዱሳን ይህንኑ ያድለን፡፡
ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ፣ 19ኛ ዓመት ቁጥር 2