መመለስ /ክፍል አንድ/

የካቲት 8 ቀን 2005 ዓ.ም.

ከእንዳለ ደምስሰ

ከቀኑ አሥራ ሁለት ስዓት ፡፡

 

ገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ስደርስ ልቦናዬን እየተፈታተነኝ ያለውን የዐሳብ ድሪቶ አውልቄ ለመጣል ትንፋሼን ሰብስቤ በረጅሙ ተነፈስኩ፡፡

 

ከተሳለምኩ በኋላ ከዋናው በር በስተግራ በኩል ካለው ዋርካ ሥር አመራሁ፡፡ የሰርክ ስብከተ ወንጌል መርሐ ግብር እየተካሄደ ነው፡፡ አካባቢዬን ቃኘሁ፡፡ ምእመናን አመቺ ነው ባሉት ቦታ ላይ ተቀምጠው የዕለቱን ትምህርት ይከታተላሉ፡፡ መምህሩ በሉቃስ ወንጌል ምዕ.15፥7 -10 ያለውን ኀይለ ቃል ከመጽሐፍ ቅዱስ እያነበቡ ነው፡፡

 

“. . . ንስሐ ከማያስፈልጋቸው ዘጠና ዘጠኙ ጻድቃን ይልቅ ንስሐ ስለሚገባ ስለ አንድ ኀጢአተኛ በሰማያት ፍጹም ደስታ ይሆናል . . . ፡፡” ሰባኪው ስብከታቸውን ቀጥለዋል . . . .፡፡

 

የሸሸግሁት ቁስል ስለተነካብኝ ውስጤ በፍርሃት ተወረረ፡፡

 

— “ማን ነገራቸው? ለዘመናት ስሸሸው የኖርኩትን የንስሐ ትምህርት ዛሬም ተከትሎኝ መጣ?” አጉረመረምኩ፡፡

 

ቀስ በቀስ ስብከቱን እያደመጥኩ ራሴን በመውቀስ ጸጸት ያንገበግበኝ ጀመር፡፡– “ለምን ስሜታዊነት ያጠቃኛል? ለምን ወደ ትክክለኛው የክርስትና ሕይወቴ አልመለስም? ዛሬ የመጨረሻዬ ይሆናል፡፡” ውሳኔዬ ቢያስደስተኝም መሸርሸሩ አይቀርም በሚል ደግሞ ሰጋሁ፡፡ ስንት ጊዜ ወስኜ ተመልሼ ታጥቦ ጭቃ ሆኛለሁ?! አንድ መቶ ጊዜ – አንድ ሺህ ጊዜ – ከዚህም በላይ . . . ፡፡ ቃለ እግዚአብሔር በሰማሁ ቁጥር ልቤ ይሰበራል፡፡ እጸጸታለሁ፡፡ ነገር ግን ከቤተ ክርስቲያኑ ቅጥር እንደወጣሁ በልቦናዬ የተተከለው ቃለ እግዚአብሔር ንፋስ እንደ ጎበኘው ገለባ ይበተናል፡፡ ውሳኔዬም ይሻራል፤ ልቦናዬ ይደነድናል፡፡ ወደ ቀድሞ እሪያነቴ እመለሳለሁ፡፡ ሁልጊዜ — “የተጠናወተኝ አጋንንት ነው እንዲህ የሚሰራኝ!” እያልኩ አሳብባለሁ፡፡

 

ሰባኪው ቀጥለዋል፡፡ “. . . አሁንም ከክፋትህ ተመለስና ንስሐ ግባ፡፡ የልቦናህንም ዐሳብ ይተውልህ እንደሆነ እግዚአብሔርን ለምን ፡፡ /የሐዋ. ሥራ ምዕ.8፥22/ ” የበለጠ ተሸበርኩ፡፡

 

አመጣጤ መምህረ ንሰሐዬ ይሆኑ ዘንድ ካሰብኳቸውና ቀጠሮ ከሰጡኝ አባት ጋር ለመገናኘት ነበር፡፡ ለመምህረ ንስሐነት በራሴ ፍላጎት ያጨኋቸው አባትም ዘገዩ፡፡ ከሶስት ቀናት በፊት ሳገኛቸው አብረን ተቀምጠን የተነጋገርንበት ቦታ ላይ ሆኜ እየጠበቅኋቸው ነው፡፡ ያገኘሁዋቸው ከሰንበት ትምህርት ቤቱ የቅርብ ጓደኛዬ ነው፡፡ ቀድሞ ከነበሩኝ የንስሐ አባቴ ጋር ስላልተግባባን፤ በተለይም ቁጣቸውን መቋቋም ስላቃተኝ ለመቀየር ወስኜ ነው የመጣሁት፡፡

 

— “ይገርማል! ስንተኛዬ ናቸው ማለት ነው? 1 – 2 – 3 . . . 4ኛ!” በአንድ ዓመት ተኩል ውስጥ ሦስት መምህረ ንስሐ ይዤ ፈርጥጫለሁ፡፡ — “ምን አይነት አባት ይሆኑ? የማይቆጡ፤ የማያደናብሩ፤ ጥቂት ብቻ ቀኖና የሚሰጡ ከሆነ ነው አብሬ የምቆየው፡፡” እንደተለመደው ለማፈግፈግ ምክንያት አዘጋጀሁ፡፡

 

መልሼ ደግሞ — “ምን አይነት ሰው ነኝ?! ዳግም ወደ ኀጢአት ላልመለስ ከራሴ ጋር እየተነጋገርኩ መልሼ እዚሁ አፈርሰዋለሁ እንዴ?! መጨከን አለብኝ፡፡ የሆነውን ሁሉ እናዘዛለሁ፡፡” ሙግቴ ቀጥሏል . . . ፡፡

 

ሰባኪው “. . . እንግዲህ ኀጢአታችሁ ይሠረይላችሁ ዘንድ ንስሐ ግቡ፤ ተመለሱም፤ ከእግዚአብሔር ዘንድ የይቅርታ ዘመን ይመጣል፡፡” የሐዋ.ሥራ ምዕ.3፥19 እያሉ በመስበክ ላይ ናቸው፡፡

 

— “ይቺ ጥይት ለእኔ የተተኮሰች ናት!” አልኩ በልቤ ሰባኪው ርዕስ እንዲቀይሩ  እየተመኘሁ ፡፡  — “እውነት ግን የይቅርታ ዘመን የሚመጣልኝ ከሆነ ለምን ከልቤ ንስሐ አልገባም? እስከ መቼ በኀጢአት ጭቃ እየተለወስኩ እዘልቀዋለሁ? መርሐ ግብሩ ይጠናቀቅ እንጂ ዝክዝክ አድርጌ ነው የምነግራቸው፡፡” ቅዱስ ጊዮርጊስን በተሰበረ ልብ ኀጢአቴን እናዘዝ ዘንድ እንዲረዳኝ ተማጸንኩት፡፡

 

ሰባኪው በቀላሉ የሚለቁኝ አይመስልም፡፡ “. . . ከእግዚአብሔር ፍርድ እንደምታመልጥ ታስባለህን? ወይስ በቸርነቱ ብዛት በመታገሱ ለአንተም እሺ በማለቱ እግዚአብሔርን አላዋቂ ልታደርገው ታስባለህን? የእግዚአብሔርንስ ቸርነቱ አንተን ወደ ንስሐ እንዲመልስ አታውቅምን? ነገር ግን ልቡናህን እንደማጽናትህ ንስሐም እንዳለመግባትህ መጠን የእግዚአብሔርን እውነተኛ ፍርዱ በሚገለጥበት ቀን ቁጣን ለራስህ ታዘጋጃለህ፡፡” ሮሜ. 2፡3-5 እያሉ በሚሰብኩት ስብከት ልቡናዬን አሸበሩት፡፡

 

— “የአሁኑ ይባስ! ዛሬ ስለ እኔ ተነግሯቸው ነው የመጡት፡፡ ወረዱብኝ እኮ!” እላለሁ፡፡ መልሼ ደግሞ  — “እውነታቸውን ነው ይበሉኝ!!” ትምህርትም ሆነ እውቀት ሳያንሰኝ ከልቤ ልመለስ አለመቻሌ አሳፈረኝ፡፡

 

በሰ/ት/ቤት ውስጥ እንደ ማደጌና ለአገልግሎት እንደ መትጋቴ ለንስሐ  ጀርባ መስጠቴ ምን የሚሉት ክርስትና ነው? ሌሎች በአርአያነት የሚመለከቱኝ፤ ‹ክርስትናን ከኖሩት አይቀር ልክ እንደ እሱ ነው!› የተባለልኝ – ነገር ግን በኃጢአት ጥቀርሻ የተሞላሁ አሳፋሪ ሰው ነኝ፡፡ ነጠላ መስቀለኛ ለብሶ፤ መድረኩን ተቆጣጥሮ መርሐ ግብር መምራት፤ ለመስበክ መንጠራራት ፤ለመዘመር መጣደፍ ፤. . . ምኑ ቀረኝ?

 

ጊዜው የጉርምስና ወቅት በመሆኑ ለኀጢአት ስራዎችም የበረታሁበት ወቅት ነው ፡፡ ሰ/ት/ቤት ውስጥ የማያቸው እኅቶቼን ሁሉ የእኔ እንዲሆኑ እመኛለሁ፡፡ ምኞት ኀጢአት መሆኑን ሳስብ ደግሞ መለስ እላለሁ፡፡ ግን ብዙም ሳልቆይ  እቀጥላለሁ፡፡ በሥራ ቦታዬ ደግሞ ማታለልን ፤ በጉልበት የሌሎችን ላብ መቀማትን ፤ ማጭበርበር የዘወትር ተግባሬ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ለአገልግሎት ስሔድ ደግሞ ሁሉን እርግፍ አድርጌ ለበጎ ስራ እተጋለሁ፡፡ — “መርዛማ ዛፍ መልካም ፍሬን ማፍራት ትችላለችን?” ራሴን እየሸነገልኩ ለጽድቅም ሆነ ለኩነኔ በረታሁ፡፡

 

አንድ ቀን በሰ/ት/ቤታችን ውስጥ በሥነ ምግባሩ የታወቀ፤ ለሌሎች አርአያ የሆነ እንደ እኔ አጭበርባሪ ነው ብዬ የማልገምተውና የማከብርው ጓደኛዬ የንስሐ አባት መያዙን ነገረኝ፡፡ እኔስ ከማን አንሳለሁ? ይመቹኛል የምላቸውን አባት መርጬ ያዝኩ፡፡ ተደሰትኩ፡፡ ቀስ በቀስ በሚኖረን ግንኙነት ኀጢአቴን ሳልደብቅ መናዘዝ ጀመርኩ፡፡ ዛሬ ቀኖና ተቀብዬ፤ ጸሎት አድርሰውልኝ በእግዚአብሔር ይፍታህ የተደመደመ ኃጢአቴን ገና ከአባቴ እንደተለየሁ እደግመዋለሁ፡፡ እንደውም አብልጬ እሰራለሁ፡፡ እናዘዛለሁ፡፡ ተመልሼ እጨቀያለሁ፡፡ የንስሐ አባቴን ትዕግስት ተፈታተንኩ፡፡ እሳቸውም አምርረው ይገሥጹኛል፡፡ ድርጊቴ ተደጋገመ፡፡ ሁኔታቸው ስላላማረኝ ሳልሰናበታቸው ጠፋሁ፡፡

 

ለሁለተኛ ጊዜ ሌላ የንስሐ አባት ያዝኩ፡፡

 

እኚህ ደግሞ በጣም እርጋታን የተላበሱ ሲሆኑ ሲመክሩኝ ደግሞ የሌሎችን ታሪክ በምሳሌነት በማንሳት ያስተምሩኛል፡፡ ቀኖና ሲሰጡኝም በትንሹ ነው፡፡ የሰራሁት ኀጢአትና የሰጡኝን ቀኖና ሳመዛዝን ኀጢአቴ ይገዝፍብኛል፡፡ የሚሸነግሉኝ ይመስለኛል፡፡

 

— “ጸሎት አታቋርጥ፤ መጻሕፍትን መድገም ትደርስበታለህ፤ በቀን ለሶስት ጊዜያት አንድ አንድ አቡነ ዘበሰማያትን ድገም፡፡ ለሕፃን ልጅ ወተት እንጂ ጥሬ አይሰጡትም፡፡ ስትጠነክር ደግሞ ከፍ እናደርገዋለን፡፡” ይሉኛል፡፡

 

የናቁኝ መሰለኝ፡፡ — “እንኳን አባታችን ሆይ እኔ ጀግናው የዘወትር ጸሎት ፤ ውዳሴ ማርያም፤ አንቀጸ ብርሃን ፤ የሰኔ ጎልጎታ፤ መዝሙረ ዳዊት፤ ሰይፈ መለኮት፤ሰይፈ ሥላሴ ጠዋትና ማታ መጸለዬን አያውቁም እንዴ?! እንዴት በአባታችን ሆይ ይገምቱኛል?” አኮረፍኩ፡፡ ጠፋሁ፡፡

 

ደግሞ ሌላ ፍለጋ፡፡

 

ሦስተኛው የንስሐ አባቴ በትንሹም በትልቁም ቁጣ ይቀናቸዋል፡፡ እንደመቆጣታቸው ሁሉ አረጋግተው ሲመክሩ ደግሞ ይመቻሉ፡፡ ነገር ግን ቁጣቸውን መቋቋም ስለተሳነኝ ከእሳቸውም ኮበለልኩ፡፡

 

ዛሬ ውሳኔዬን ማክበር አለብኝ፡፡ ወደ ልቦናዬ መመለስ፡፡ በሉቃስ ወንጌል ምዕ. 15 ላይ እንደተጠቀሰው የጠፋው ልጅ፡፡ ወደ አባቴ ቤት በቁርጠኝነት መመለስ፡፡ ልጅ ተብዬ ሳይሆን ከባሪያዎች እንደ አንዱ እቆጠር ዘንድ፡፡

 

ከምሽቱ 12፡30 ሆኗል፡፡

 

ሰባኪው አሰቀድሞ ይሰጡት የነበረውን የንስሐ ትምህርት ቀጥለዋል፡፡  “. . . በተመረጠችው ቀን ሰማሁህ፤ በማዳንም ቀን ረዳሁህ፤ እነሆ የተመረጠችው ቀን ዛሬ ናት፡፡” 2ኛ ቆሮ. ምዕ› 6፡2 እያሉ ቃለ እግዚአብሔርን በምዕመናን ልቦና ላይ ይዘራሉ፡፡

 

— “እውነትም ለእኔ የተመረጠችው ቀን ዛሬ ናት፡፡ አምላኬ ሆይ ኃይልና ብርታትን ስጠኝ፡፡ ወደ ትክክለኛው አእምሮዬ እመለስ ዘንድ፤ በኀጢአት የኖርኩበት ያለፈው ዘመን ይበቃ ዘንድ እርዳኝ!!” አልኩ የተፍረከረከውን ልቦናዬ ያጸናልኝ ዘንድ እየተመኘሁ፡፡

 

— “አሁን ምንድነው ማድረግ ያለብኝ? እ – በመጀመሪያ ራሴን ማረጋጋት፡፡ ከዚያም እሰከ ዛሬ የፈጸምኩትን የኃጢአት ኮተት ማሰብ ፤ በመጨረሻም አንኳር የሆኑትን መናዘዝ፡፡” አልኩ ህሊናዬን ለመሰብሰብ እየጣርኩኝ፡፡

 

— “ግን እኮ የኀጢአት ትንሽ እንደሌለው ተምሬያለሁ፡፡ስለዚህ ሸክሜን ሁሉ ለመምህረ ንስሐዬ መናዘዝ አለብኝ፡፡” ውሳኔ ላይ ደረስኩ፡፡

 

ኀጢአት ናቸው ብዬ በራሴ አእምሮ የመዘንኳቸውን አስቦ መጨረስ አቃተኝ፡፡ በድርጊቴ ተገርሜ — “በቃ የኀጢአት ጎተራ ሆኛለሁ ማለት ነው? መቼ ይሆን ሰንኮፉ የሚነቀለው? እባክህ አምላኬ በቃህ በለኝ!”  ኃጢአቴን ማሰብ አደከመኝ፡፡

 

የዕለቱ የሰርክ ጉባኤ እንደተጠናቀቀ አበ ንስሐ ይሆኑኝ ዘንድ ቀጠሮ ያስያዝኳቸው አባት በመጠባበቅ አይኖቼ ተንከራተቱ፡፡

 

— “ረስተውኝ ይሆን እንዴ? – እውነታቸውን ነው – እኔ መረሳት ያለብኝ ሰው ነኝ፡፡ ለምንም – ለማንም የማልጠቅም ከንቱ ሆኛለሁ፡፡ ኀጢአት ያጎበጠኝ ምናምንቴ ነኝ!! የኀጢአት ሸክሜን የማራግፍበት ፍለጋ በመባዘን እሰከ መቼ እዘልቀዋለሁ? እውነተኛ ንስሐ መግባት ተስኖኝ እስከ መቼ እቅበዘበዛለሁ?” የዕንባ ጎተራዬ ተከፈተ፡፡ ከዓይኔ ሳይሆን ከልቤ ይመነጫል፡፡ መጨረሻዬ ናፈቀኝ፡፡

 

“እንደምን አመሸህ ልጄ?” አሉኝ የቀጠርኳቸው አባት ጭንቅላቴን በመስቀላቸው እየዳበሱኝ፡፡

 

ዕንባዬ ያለማቋረጥ እየወረደ ቀና ብዬ ተመለከትኳቸው፡፡ ከተቀመጥኩበት ተነስቼ መስቀል ተሳለምኩኝ፡፡ በሃምሳዎቹ የዕድሜ ክልል ውስጥ የሚገኙ አባት ናቸው፡፡ ገብስማ ሪዛቸው ግርማ ሞገስ አላብሷቸዋል፡፡

 

“ምነው አለቀስክ?” አሉኝ አጠገቤ ካለው ጠፍጣፋ ድንጋይ ላይ እየተቀመጡ፡፡

 

ሳግ እየተናነቀኝ “ሸ- ሸ – ክሜ ከ- ከ-ብ-ብዶ-ብብ-ኝ ነው አባቴ! ም- ምንም  የማ- ማልጠቅም ሆኛለሁ!!” አልኳቸው ሆድ ብሶኝ፡፡

 

“መጸጸት መልካም ነው፡፡ ጸጸት ጥንካሬን ይወልዳል ልጄ! አይዞህ፡፡” አሉኝ በጥልቀት እየተመለከቱኝ፡፡

 

— “እግዚአብሔር ረድቶኝ የመጨረሻዬ ቢሆን ጥሩ ነበር፡፡” አባባላቸውን ተመኘሁት፡፡

 

— ‹‹አምላኬ ሆይ ብርታትን ስጠኝ፡፡ ውስጤ የታመቀውን የኃጢአት ጥቀርሻ ይታጠብ ዘንድ፤ የሆነውን ሁሉ በተሰበረ መንፈስ እናዘዝ ዘንደ እርዳኝ፡፡›› አልኩኝ ለራሴ፡፡ ቀና ብዬ አያቸው ዘንድ ብርታት አጣሁ፡፡

 

“ስመ ክርስትናህ ወልደ ሚካኤል ነው ያልከኝ?”

 

“አዎ አባቴ!”

 

“ሰሞኑን ስንገናኝ ከንስሐ ልጆቼ ጋር ጉዳይ ይዘን ስለነበር ጉዳይህን አልነገርከኝም፡፡ ለምን ይሆን የፈለግኸኝ?”

 

“አባቴ በቀጠሯችን መሠረት መጥቻለሁ፡፡ በኀጢአት ምክንያት የተቅበዘበዝኩኝ፤ ኀጢአቴ ያሳደደኝ፤ ለዓለም እጄን የሰጠሁ ምስኪን ነኝ፡፡ ህሊናዬ ሰላም አጥቷል፡፡ ያሳርፉኝ ዘንድ አባትነትዎን ሽቼ ነው የመጣሁት፡፡” አልኳቸው በተሰበረ ልሳን፡፡

 

ለጥቂት ሰከንዶች ከራሳቸው ጋር የሚመክሩ በሚመስል ስሜት ቆይተው “ልጄ የንስሐ ልጆች በብዛት አሉኝ፡፡ ሁሉንም ለማዳረስ አልቻልኩም እኔም በፈተና ውስጥ ነኝ፡፡ አንተ ደግሞ ተጨምረህ ባለ እዳ ሆኜ እንዳልቀር ሰጋሁ፡፡ ይቅርታ አድርግልኝና ሌላ አባት ብትፈልግ ይሻላል፡፡” አሉኝ ትህትና በተላበሰ አነጋገር፡፡

 

“እግዚአብሔር እርስዎን አገናኝቶኛልና ወደ ሌላ ወዴትም አልሔድም፡፡ ያለፈው ይበቃኛል፡፡” አነጋገሬ ውሳኔዬን እንደማልቀይር ይገልጽ ነበር፡፡

 

“ያመረርክ ትመስላለህ፡፡” አሉኝ ውሳኔዬ አስገርሟቸው፡፡

 

“አባቴ ታከተኝ፡፡ ቆሜ ስሔድ ሰው እመስላለሁ ፤ ነገር ግን ኀጢአት በባርነት የገዛኝ ርኩስ ነኝ፡፡ የመጣሁት ከባርነት ይታደጉኝ ዘንድ ነው፡፡ እባክዎ አባቴ እሺ ይበሉኝ!” ስቅስቅ ብዬ አለቀስኩ፡፡

 

ለቅሶዬን እስክገታና አስክረጋጋ ድረስ ጠብቀው “እንዲህ በተሰበረ መንፈስ ውሰጥ ሆነህ ጥዬህ ብሄድ ሸክሙ ለራሴው ነው፡፡ አንድ ጊዜ መጥተሃልና አላሰናክልህም፡፡” አሉኝ በፍቅር እያስተዋሉኝ፡፡

 

“እግዚአብሔር ይስጥልኝ አባቴ!” እግራቸው ላይ ተደፋሁ፡፡

 

“ተው – ተው አይገባም ልጄ – ቀና በል፡፡” ብለው ከተደፋሁበት በሁለት እጃቸው አነሱኝ፡፡

 

“ከዚህ በፊት አበ ነፍስ ነበረህ?” አሉኝ አረጋግተው ካስቀመጡኝ በኋላ፡፡

 

በአዎንታ ጭንቅላቴን ከፍና ዝቅ በማድረግ ገለጽኩላቸው፡፡

 

“በምን ምክንያት ተለያያችሁ?”

 

ራሴን ለማረጋገት እየሞከርኩ ዕንባዬን ጠርጌ በረጅሙ ተነፈስኩ፡፡

 

“አባቴ ታሪኩ ብዙ ነው፡፡ ከአንድም ሦስት ጊዜ የንስሐ አባት ቀያይሬያለሁ፡፡”

 

“ለምን?” በመገረም ነበር የጠየቁኝ፡፡

 

“ለእኔም እንቆቅልሽ ነው፡፡ ከአንዱ እየፈረረጠጥኩ ወደ አንዱ እየሔድኩ ነፍሴን አሳሯን አበላኋት፡፡”

 

“ከሦስቱም እየተሰናበትክ ነው እዚህ የደርስከው?” የበለጠ ለመስማት በመጓጓት ጠየቁኝ፡፡

 

“ከአንዳቸውም ጋር በስንብት አልተለያየሁም፡፡ በራሴ ፈቃድ ኮበለልኩ፡፡”

 

ለውሳኔ የተቸገሩ በሚመስል ስሜት የእጅ መስቀላቸውን እያገላበጡ ተከዙ፡፡ በመካካላችን ጸጥታ ሰፈነ. . . ፡፡

ይቀጥላል

gubae

የሥነ ጽሑፍ ውድድር

gubae

ቅዱስ ጳውሎስ

ከዲ/ን መስፍን ደበበ
እርሱ እናቴ እኔን ቅሪት እያማጠኝ፤
በልጅነት ሊገላገል በሐሳብ ያረገዘኝ፤
በማኅፀን ሰፋድሉ በትምህርቱ እኔን ስሎ፤
በመዶሻው እኔን ጠርቦ አስተካክሎ፤
እጄን ይዘህ አለማምደህ እንዲያ ስድህ፤
ቃለ ነገር ቃለ ምሥጢር እየጋትህ፤
ጠንካራውን ጥሬ ቃሉን አስቆርጥመህ፤
አንተ አብይ ባሕር የትምህርት ውቅያኖስ፤
ምርጥ ዕቃ ማዕዘን ዕብነ አድማስ፤
በእንቁላል ቅርፊት ቀድቼ የረካሁኝ ከአንደበትህ፤
ርዕሰ እውቀት አንተ አፈ ዝናም በትምህርትህ፡፡
አሕዛበ-ምድር ማንነቴን በጠብታህ ጎበኘሃት፤
የነፍሴን እርሻ አጥግበህ በልምላሜ ከደንካት፡፡
ሕሊናዬን በተመስጦ መንኮርኩር ስታከንፋት፤
ከታችኛው ከእንጡረጦስ ከበርባኖስ ስታጠልቃት፤
ዖፈ ጣጡስ መጥቀህ በረህ የነገርኸኝ፤
እንደ ሙሴ ከእግረ ታቦር ያላቆምኸኝ፤
አለማወቅ ጥቁር ካባ፤ የጨለማን መጋረጃን ያራቅህልኝ፤
ኢትትሃየድ እያለ ወራሴን ስታለምደኝ፤
ምሥጢሩን ስትቀዳ ዘቦቱን ስትነግረኝ፤
የሰብዕና ዘበኛዬ እኔን በትምህርቱ ንቅሳት ሲነትበኝ፤
ያኔ ነበር የነቀሰኝ በልቡናዬ ሕያው ቃሉን የከተበኝ፤
በጉልጓሎ በእርሻው ቦታ የጠመደኝ፤
እያረሰ ጅራፍ ቃሉን ጆሮዬ ላይ ሲያጮህብኝ፤
ከሃያው ክንድ ከመቅደሱ ከሚፈልቀው፤
ከዙፋኑ ከቃል ሥግው ከሚፈሰው፤
እንደ መስኖ ሊቀላቀል ከሚወርደው፤
ከእኔ ሕይወት ከሸለቆ ከአዘቅቱ ሲንዶሎዶል፤
የመብል ዛፍ ፍሬ በኩር ሲያበቅል፤
ያኔ ነበር ስሜ ሽቶ ከጌታ ስም ሲቀላቀል፤
ሃይማኖት የፍቅር እሳት ሲንቀለቀል፤
ተቆጠርኩኝ ግብር ገባሁ ከቤተ ወንጌል፡፡

አበው ይናገሩ

ዘርዓቡሩክ ገ/ሕይወት
ቀን መስከረም 11/2004 ዓ.ም

እስኪ ቀስቅሷቸው አበው ይናገሩ
የምንኩስና ግብር ምን ነበር ምሥጢሩ
የክርስትና ሕይወት ምን ነበር ተግባሩ
መቃብሩን ክፈቱና አበው ይመስክሩ፡፡
እኔስ ሰው አማረኝ የሃይማኖት ጀግና
ወልድ ዋሕድ ብሎ በእምነቱ የፀና
ጀግና ሰው አማረኝ ጠላት አሳፋሪ
ንጽህት ድንግል ብሎ እምነቱን መስካሪ፡፡
ነብያት በመጋዝ የተሰነጠቁት
ሐዋርያት ቁልቁል የተዘቀዘቁት
ሰማዕታት በእሳት የተለበለቡት
ቅዱሳን በገዳም ደርቀው የተገኙት
ምሥጢሩ ምን ነበር? አበው ይናገሩት፡፡
ይናገር ዝቋላ ግሸን ላሊበላ
የቅዱሳንን ዐፅም ለምን እንዳልበላ፡፡
ዋልድባ ይናገር ዜጋመልም ሳይቀር
እንባቸው መፍሰሱ ለምን እንደነበር፡፡
ነበር ወይ ፈልገው ሹመት ሽልማት?
ወይስ ሀብት ንብረት የተሟላ ቤት?
ወይስ አምሯቸው ነው ፈልገው መሞት?
እናንተ ገዳማት ምሥጢሩን አውሩት፡፡
ጐበዝ ሰው አማረኝ በእምነቱ የፀና
ምግባር ሃይማኖቱ በእጅጉ የቀና፡፡
እንጦንስ የወለደው በምግባር በእምነት
ተምሮ ያደገ ከተክለሃይማኖት፡፡
የጊዮርጊስ ወገን የት ነው የማገኘው?
በመሀል ከተማ በአራዳ ውስጥ ነው?
ወይስ በዝቋላ በደብረ ሊባኖስ በደብረ ዳሞ ነው?
ወገን ሰው ናፈቀኝ ዐይኔን ሰው አማረው
የሃይማኖት ጀግና የትነው የማገኘው?
ልግባ ወይ ዋልድባ ጫካ ካለበት
ማኅበረ ሥላሴ ከቅዱሳን ቤት?
አክሱም ግሸን ማርያም ከቃል ኪዳን ቦታ
ይገኛል ወይ ጀግና ጠላት የሚረታ?
ፈሪሐ እግዚአብሔር በልቡ ያደረ
ቤተ ክርስቲያንን ያልተደፋፈረ፡፡
የት ነው የማገኘው ለሃይማኖቱ ሟች
ለተዋሕዶ እምነት ጠበቃ ተሟጋች፡፡
የወገን መመኪያ የከሀዲ መቅሰፍት
ማነው እሱ ጀግና ተኝቶ እንደሆነ ይነሣ ቀስቅሱት፡፡
እስኪ ቀስቅሷቸው አበው ይናገሩ
የምንኩስና ግብ ምን ነበር ምሥጢሩ?
የክርስቲያን ሕይወት ምን ነበር ተግባሩ?
መቃብሩን ክፈቱት አበው ይመስክሩ፡፡
ወገን ሰው ናፈቀኝ ዐይኔን ጀግና አማረው
በእምነቱ የፀና የትነው የማገኘው?
ብቅ ይበል እንየው እሱ ማነው ጀግና?
በጐችን ከተኩላ ነቅቶ የሚጠብቅ
መከራ ቢከበው ከቶ የማይሰቀቅ
የሃይማኖት ጀግና ቆራጥ ሰው ገበሬ
እንደዚያ እንደ ጥንቱ ይገኛል ወይ ዛሬ?
የወገን የዘመድ ጥቅም ያላወረው
የመናፍቆች እጅ ኪሱን ያልዳበሰው
የዓለም አሸክላ ልቡን ያልማረከው
የክርስቶስ ወዳጅ እሱ ጀግና ማነው?
ምሥጢርን ከምሥጢሩ አንድ አድርጐ ቀምሮ
ወልድ ዋሕድ ብሎ ሃይማኖት መስክሮ
እንጦንስን መቃርስን በልቡ ያኖረ
ከአትናቴዎስ ከቄርሎስ ጥበብ የተማረ፡፡
ድንግል እመቤቴ ብሎ የሚመሰክር
መሆኗን የሚያምን ማኅደረ እግዚአብሔር
ቋቅ እንትፍ ብሎ የጠላ ክህደትን
ትንታግ ምላስም ጭንግፍግፉን
ልሳነ ጤዛ መናፍቅን
ወልደ አርዮስ ዲቃላውን፡፡
በሰይፈ ሥላሴ የሚቀላ
ጀግና ማነው ዝቅ ይበላ፡፡
ነበር ወይ ያን ጊዜ ለሹመት መጓጓት
እስኪ ጎርጎርዮሰ ይምጣና ጠይቁት
ፍቅርንም ይጠየቅ አባ ሕርያቆስ
ምሥጢርን ጠባቂ ወይም አባ መቃርስ፡፡
የክርስቶስ ባርያ የአጋንንት መቅሰፍት
ወንጌል አስተማሪ የሃይማኖት አባት
ይህንን ጉድ እንዲያይ ይምጣ ተክለሃይማኖት
የጸሎት ገበሬ ገብረ መንፈስ ቅዱስንም ይነሣ ቀስቅሱት
ይነሣ ጊዮርጊስ ይመስክር ምሥጢር
የሃይማኖት ፍቅር ምን እንደነበር፡፡
ከእናቶቻችንም አሉ ለፍጥረት ያዘኑ
ዲያብሎስ እንዲማር ጌታን የለመኑ፡፡
ስንቱን ልዘርዝረው የአባቶችን ሙያ
መር ብለው የወጡት ከሥጋ ገበያ
ጾም ጸሎት ነበረ የሃይማኖት ጋሻ
መልከስከስ ምንድነው እንደ አበደ ውሻ፡፡
እንደ መስኖ ውሃ ከነዱት መነዳት
ዓላማው ምንድነው የዘመኑ ወጣት፡፡
እኔስ ሰው አማረኝ የሃይማኖት ጀግና
ወልድ ዋሕድ ብሎ በእምነቱ የፀና
ዐይኔን ሰው አማረው ጀግና ሰው ገበሬ
ሃይማኖት መስካሪ እንደ ጥንቱ ዛሬ፡፡

ምንጭ፡- መለከት 1ኛ ዓመት ቁጥር 6

የአባቴ ተረቶች

ሕይወት ቦጋለ

ሐምሌ 16/2003 ዓ.ም.

 
ሌሊቱን ለረጅም ሰዓታት የዘነበው ዝናብ አባርቶ ቦታውን ለንጋት አብሳሪዋ ፀሐይ ከለቀቀ ቆየት ብሏል፡፡
ከመኝታዬ የተነሣሁት አረፋፍጄ ቢሆንም አሁንም የመኝታ ቤቴን መስኮት ከፍቼ አውራ መንገዱን እየቃኘሁ ነው፡፡ ለምን እንደሆነ ባላውቅም ዘወትር ከእንቅልፌ ስነሣ ሰፈራችን ሰላም ለመሆኗ ማረጋገጫዬ የመኝታ ቤቴ መስኮት ናት፡፡
ሁሉም ወደየ ጉዳዩ እንደየ ሐሳቡ መለስ ቀለስ ይለዋል፡፡ የቸኮለ ይሮጣል፣ ቀደም ብሎ የተነሣው ዘና ብሎ ይራመዳል፡፡ ሥራ ፈቱ ይንገላወድበታል ብቻ መንገዱ ለሁሉም ያው መንገድ ነው፡፡ እንደ እኔ ላጤነው ከቁም ነገር ቆጥሮ ላየው ደግሞ ለዓይን ወይም ለአእምሮ የሚሆን አንድ ጉዳይ አይታጣበትም፡፡ ያባቴን ተረቶች ናፋቂ ነኝና ወደሳሎን ወጣሁ፡፡

“አቤቱ ቃሌን አድምጥ፣
ጩኸቴንም አስተውል፣
የልመናዬን ቃል አድምጥ፣
ንጉሤና አምላኬ ሆይ
አቤቱ ወደ አንተ እጸልያለሁና
በማለዳ ቃሌን ስማኝ፤
በማለዳ ፊትህ እቆማለሁ…”

አባቴ አሁንም የጠዋት ጸሎቱን አልጨረሰም እናቴ ደግሞ እንደወትሮዋ ቁርስ ለማዘጋጀት ተፍ… ተፍ እያለች ነው፡፡ ከእናቴ ፈጣንና ፍልቅልቅነት ጋር ያባቴ የእርጋታና የዝምተኝነት ባህሪ ተስማምቶ መኖሩ የሚገርመኝ ነገር ነው፡፡ ለነገሩ “ዓለም የተቃራኒ ነገሮች ድምር ውጤት ናት” ይላል አንድ ስሙ የጠፋኝ ፈላስፋ፡፡
አባቴ ጸሎቱን ጨርሶ ወደ ቤት ዘልቆ አሮጌው ሶፋ ላይ ተቀምጧል፡፡

“እንደምን አደርክ አባባ”
እግዚአብሔር ይመስገን ልጄ አንቺስ እንዴት አደርሽ?”

እናቴ ቁርስ አቅርባለች እኔም ዘወትር እንደማደርገው ከአባቴ እግር ስር ቁጭ ብዬ ጉርሻውን እየተቀበልኩ ቁርሴን እየበላሁ ነው፡፡
በአባቴ የሚነገሩ ታሪኮችና ተረቶች ከኋላቸው የሚያስከትሉትን ምክሮችና ቁም ነገሮችን ሳስብ እነዚህ ቱባ እውቀቶች ለሁሉም ቢደርሱ እንዴት ይጠቅሙ ነበር አያልኩ አስባለሁ፡፡
ዘወትር ከአባቴ የምከትባቸውን ተረቶች መጽሐፍ ለማድረግ ድንገት ሐሳቡ በአእምሮዬ ሽው ያለ እንደሆን ከእጅ ወደ አፍ የሆነውን የኛን ቤት ኑሮ አስታውሼ ተስፋ እቆርጣለሁ፡፡

“ጎሽ ልጄ የሚጠጣ ውሃ በጠርሙስ ሞልተሽ አምጭልኝ” የሚለው ያባቴ ትእዛዝ ከገባሁበት የሐሳብ ማዕበል መንጥቆ አወጣኝ፡፡
“የሚሚዬ አባት ለሚካኤል የጠመኩት ጠላ እኮ አላለቀም.. ከሱ ይጠጡ” እናቴ ነበረች፡፡
“ከዘንድሮስ ጠላ ውሃው ይሻለኛል ተይው” የሚለውን ያባቴን ምላሽ ስሰማ አባቴ በዘንድሮ ላይ ያለው ምሬት የተለየ መሆኑ እየገረመኝ ውሃውን አቀረብኩለት፡፡
“እሰይ እሰይ! እሰይ!” እያለ ጥሙን ይቆርጣል፡፡

“በአባቶቻችን ጊዜ ብዙ ሠርቶ እንዳልሠራ የሚሆን ሰው ማግኘት ቀላል ነበር፡፡ ስለ ብቁና ጎበዝ ሰው ምስክሩ ሥራው ብቻ ነበር ልጄ፡፡ ቢሆንም የዝና ናፋቂዎች ጥቂቶች አልነበሩም፡፡ ብዙኃኑ ግን ያለ አግባብ ሙገሳን እንደ ስድብ እንቆጥር ነበር፡፡ እከሌ እኮ ጀግና ነው ቢሉን ስለ ጀግንነቱ ማረጋገጫ ከእርሱው እንጂ በዝናው አናምንም ነበር፡፡

“ልጄ ዘንድሮ በዓይን የሚታይ በጎ ሥራ ጠፋ፤ እስቲ ከዓይን ተርፎ ልብን የሚሞላ ተግባር የሠራውን ሰው አሳይኝ?”  ድንገተኛው ያባቴ ጥያቄ አስደነገጠኝ፡፡ አባቴ የከበደኝን ጥያቄ ከኔ ምላሽ ሳይጠብቅ መንገሩን ቀጠለ፡፡

“ዘንድሮ ጥቂት ተሠርቶ ለስምና ለዝና የሚሮጥበት ጊዜ ነው፡፡ ከተግባር ስም የቀደመበት የውዳሴ ከንቱ ዘመን፡፡” እያለ አባቴ መናገሩን ቀጠለ፡፡ “ልጄ ስላንቺ ተግባርሽ እንጂ ዝናሽ አይመስክር” የምትለዋን የዘወትር ንግግሩን አስተውያት ባላውቅም ዘወትር መስማቴን አስታውሳለሁ የዛሬው አባቴ ገፅታ ከወትሮው በተለየ መልኩ ትካዜና ደስታ አልባ ሆኗል፡፡

ምን ሊመክረኝ ይሆን እያልኩ ወደ ጉልበቱ ተጠጋሁ

“ከአባቶቻችን ሐዋርያት ትሕትናን፣ ባለብዙ ዕውቀት ሆነው እንዳላወቁ፤ ባለጸጋ ሆነው እንዳልሆኑ መምሰልን መማር ይገባናል ልጄ ስም ከሥራ መቅደም የለበትም ልጄ…”

ቀበሮ ሥጋ በአፏ የያዘች ቁራ ትመለከትና ከመሬት ሆና “እሜት ቁራ ከአእዋፍ መካከል እንዳንቺ ያለ ውብና ቆንጆ፤ አስተዋይና ባለ አእምሮ የለም” እያለች ታሞግሳት ጀመር፡፡የቁራን ዝምታ ያልወደደችው እሜት ቀበሮ ውዳሴዋን ግን አላቆመችም

“እሜት ቁራ ሆይ በምድር ለሚገ አእዋፍ ሁሉ ንግሥት የምትሆን ፈለግን፤ በምድር ሁሉ ዞርን ግን አላገኘንም ድንገት አንቺን አየን፡፡ በዚህ ውበትሽ ላይ ድምፅሽ ቢያምር አንቺን ለንግሥትነት እንመርጥሻለንና እስቲ ድምፅሽን አሰሚኝ አለች ቀበሮ”

ንግሥት ለመሆን የተመኘችው ቁራ በቀበሮ ሙገሳ ተታላ “ቁኢኢ..” ብላ ብትጮኸ የነከሰችው ሥጋ ወደቀ፡፡ ያሰበችው የተሳካላት እመት ቀበሮ “በዚህ ድምፅና ውበት ላይ ማስተዋል ቢጨመርበት ኖሮ እንዳንቺ ያለ የአእዋፍ ንግሥት እግር እስኪነቃ ቢኬድ አይገኝም ነበር” ብላ ተመጻደቀችባት ይባላል፡፡

ልጄ ስንቱ በውዳሴ ከንቱ ጸጋውን ተነጥቆ ከክብር ተዋርዶ ይሆን? የሰው ስስ ብልት ዝና ናፋቂ መሆኑን የተገነዘበው ዲያብሎስም እንደ ልቡ እየተጫወተብን ነው፡፡ ስንት የት ይደርሳሉ የተባሉ ሰዎች ካቅማቸው በላይ ባገኙት ዝና ተልፈስፍሰው ከእርምጃው ተገተው ይሆን?

ውሃ የሞላ ብርጭቆውን አነሣና ተጎነጨለት

እሰይ! ይኸውልሽ ልጄ ለሰው ውድቀቱ ውዳሴ ከንቱ ነው፡፡ ምእመናን ጥቂት መንፈሳዊ አገልግሎት ሠርተው የበቁ የሚመስላቸው፤ አገልግለው የማንጠቅም ባሪያዎች ነን የሚሉ እንዳልነበሩ፤ ትንሽ አስተምረው /አገልግለው/ ታይታን የሚፈልጉ አገልጋዮች በቤተ ክርስቲያናችን ሞሉ፡፡ ታዲያ ትውልድ ምን ይማር ልጄ?

ለእናት ሀገሩ በቅንነት ከመሥራት ይልቅ ሀብቷን የሚቀራመታት ለድሆች ከቆመው ይልቅ ያለ አግባብ ኪሱን በጉቦ ያደለበው ስሙ ሲገን ከማየት የደለበ ምን የሚያሳዝን ነገር አለ?

ከአባቴ አንደበት የሚወጡት ቃላት ፍላጻቸው ለልቤ ደርሰው አእምሮዬን ሲሞሉት ራሴን ዘወትር ብወቅስም ያለመለወጤ አናደደኝ፡፡

“ብዙ መሥራት የሚችለው ወጣት ተጧሪ ሆነ ለኔ የሚገባኝ ከመሥራት ይልቅ መዝናናትና በሱስ መጠመድ ብቻ ነው ብሎ የሚያስብ ነው የበዛው ልጄ..”

ከአባቴ ተረት ውስጥ ራሴን መመልከት ጀመርኩ ሁሌም አንድ ተጨባጭ ነገር ላይ መድረስ ሲያቅተኝ ልኬቴ እዚህ ድረስ ነው ብዬ ሳምን፤ በራሴ መጠራጠር ጀምሬ ነበር፡፡ ትእግስት በስሜቴ ውስጥ ሲገረጅፍ ደግሞ ግን ለምን የሚለኝ አእምሮዬ ውድቀቴን ያለ ሥራና ያለ መልካም ምግባር ዛሬም በአባቴ  ቤት ተጧሪ መሆኔን አከበደብኝ፡፡

ለስማቸው የሚጨነቁት ጥቂት ሠርተው ብዙ ስም ፈለጉ እኔ ግን ያለ ሥራ ቁጭ ብያለሁ፡፡ እስከ ዛሬ የአባቴ ተረቶች እውነታቸው ከማስበው በተለየ ዘልቆ ሲታወቀኝ፣ ጠልቆ ሲዳሰሰኝ፣ ርቆም ሲታየኝ፣ ቀርቤም ሆኖ ብዥ ሲልብኝ ኖሬያለሁ፡፡ ዛሬ ግን ራሴን ተመለከትኩ፡፡

ከአባቴ ተረቶች መሠረት ዛሬ ላይ ሆኖ ትናነትን ከመናፈቅ ይልቅ የዛሬን የተግባር ሰው መሆን እንደሚገባኝ ተገነዘብኩ፡፡ የአባቴ ቃላት ተራ ተረቶች መስለውኝ ቢኖሩም ዛሬ ግን ተጨባጭ በሆነው ዓለም ውስጥ እንዴት መኖር እንደሚገባኝ ሲጠቁሙኝ የኖሩ የተዋቡ ምክሮች ናቸው፡፡ አባቴ በኋሊት መነጽር ትናንትን የሚያሰቃኘኝ የተግባር ሰው በውዳሴ ከንቱ ያልተበገረች ጠንካራ ሠራተኛ ጥሩ መንፈሳዊ ሰው እንድሆን ነው፡፡

አሁን አባቴ ካጠገቤ ተነሥቶ በረንዳ ላይ ተቀምጧል ዓይኖቹን ቡዝዝ አድርሀጎ የፊት ለፊቱን ያያል፡፡ እኔ ግን ዓይኖቹ በትውስታ ፈረስ ትናንትን፤ የሱን ዘመን እያሰቃኙት ይመስለኛል፡፡

የሱ በትናንት ዘመን መኖርና የድሮ ተረቶቹ ከተዘፈቅሁበት ከንቱነት ከግድ የለሽነትና ከተመጻዳቂነት የሚያወጡኝ የማንቂያ ደውሎች ናቸው ለካ!! አልኩ፡፡

ለወትሮው ሠርቼ ራሱን ከመለወጥ ይልቅ ሀብታም የትዳር ጓደኛና ዝና ፈላጊነቴ ገዝፎ አእምሮዬን የሞላኝ ነበርኩ፡፡ ለዚህ ነው ከሁሉም ነገር ውስጥ ሳልሆን ጠባቂ ሆኜ መኖሬ እስከ አሁን ከልብ ሳልሆን በማስታወሻ ደብተሬ ላይ የከተብኳቸውን በርካታ ያባቴን ተረቶች መልሼ ማንበብ እንደሚጠቅመኝ አሰብኩ፡፡

“ልጄ?”

አቤት አባባ

አሁን እንግዲህ 34 ዓመት ሞላሽ አይደል?

አዎን አባባ

አባቴ ከዚህ በላይ አልጠየቀኝም መልእክቱ ገብቶኛል ትንሽ ለሀገርሽና ለቤተ ክርስቲያንሽ የሚሆን በጎ ሥራ ሳትሠሪ ጊዜ ቀድሞሻል ማለቱ ነው፡፡

አባዬ?

“አቤት ልጄ”

ለካ እስካሁን ከኖሩት ተርታ አልተመደብኩም?

“እንደሱ ነው ልጄ እንደሱ!!

/ምንጭ፡- ሐመር 18ኛ ዓመት ቁጥር 5

 

 

“የሚያየኝን አየሁት”

በትዕግሥት ታፈረ ሞላ

 04/11/2003

የክረምት ብርድ በተለያየ ምክንያት ከቤቱ የወጣውን መንገደኛ ፊት አጨፍግጎታል፡፡ ሰጥ አርጋቸው ደርጉም ከቡድኖቹ ጋር የዕለት እንጀራውን ለመጋገር ታክሲ ውስጥ ገብቷል፡፡ እሱም ሆነ ጓደኞቹ የማውራት ፍላጎት የላቸውም፡፡ ሌሊት በእርሱ አጠራር “ግዳጅ” የሚሉት የተደራጀ የሌብነት ሥራ ሲሠሩ ስላደሩ እንቅልፍ በማጣት ዐይኖቻቸው ቀልተው አብጠዋል፡፡ የወረዛው የታክሲው መስታወት ላይ የእነሱ ትንፋሽ ተጨምሮበት በጉም ውስጥ የሚሔዱ አስመሰላቸው፡፡

“ወራጅ” አለ፤ ሰጥ አርጋቸው፤ መስታወቱን በእጁ ጠረግ ጠረግ አድርጎ ወደ ውጭ እየተመለከተ፡፡ እጁ ላይ ውፍረቱ እጅግ የሚደንቅ የወርቅ ካቴና አድርጓል፡፡ ባለታክሲው ቅዱስ ጴጥሮስ ወጳውሎስ ቤተ ክርስቲያን የተሰበሰበው ሕዝብ ግርግር ስለፈጠረበት አለፍ አድርጎ አወረዳቸው፡፡ ስድስት ወንዶችና ሁለት ነጠላ መስቀለኛ ያጣፉ ሴቶች እንደኮማንደር በየተራ ዱብ ዱብ አሉና ሰጥ አርጋቸውን ከበቡት፡፡ 

“ሄይ! ጊዜ አናጥፋ፤ ባለፈው ዓመት እንዳደረግነው ቶሎ ቶሎ ሒሳባችንን ዘግተን ውልቅ፡፡” ሲል፤ አንደኛዋ ሴት “አዎ በእናታችሁ መታ መታ እናድርግና ከዚህ እንጥፋ፤ ዛሬ የምንቅመው ጫት መቼም…” ስትል የቡድኑ መሪ አቋረጣትና “ዲሞትፈርሽን ይዘሻል?” አላት፡፡ በነጠላዋ ደብቃ ስለቷ የበዛ ትንሽ ምላጭ በኩራት አሳየችው፡፡ “በቃ እኔ አምና ከቆምኩበት ከመቃብር ቤቱ ጎን እቆማለሁ፡፡ ዕቃ ከበዛባችሁ እያመጣችሁ አስቀምጡ፡፡ የቡድናችንን ሕግ በየትኛውም ደቂቃ እንዳትረሱ፡፡” አላቸው፡፡ ሕጉ ከመካከላቸው አንድ ሰው ቀን ጥሎት ቢያዝ፤ ብቻውን ይወጣዋል፡፡ ስለቡድኑ መረጃ ከመስጠት ይልቅ አንገቱን ለሰይፍ ቢሰጥ ይመርጣል፡፡ 

ሰጥ አርጋቸው ረጋ ባለ ድምፅ “ዳይ… ዳይ እግዚአብሔር ይርዳን” ሲላቸው ሁሉም ወደ ቤተ ክርስቲያኑ እግራቸውን አፈጠኑ፡፡ እሱም ከኋላቸው የጨዋ መልክ ተላብሶ ተከተላቸው፡፡ የእጁን ካቴና፣ የአንገቱን ገመድ መሳይ ሀብል ያየ ሁሉ ለእሱ በመስጋት ያዩታል፡፡ ሐሳባቸውን ቢረዳ “ሌባን ሌባ ቢሰርቀው ምን ይደንቀው” የሚለውን ተረት ይተርትባቸው ነበር፡፡ 

ቅዳሴው አልቶ ታቦት እየወጣ ነው፡፡ እልልታው ይቀልጣል፡፡ ወንዶች ፊታቸውን አብርተው ወደ መድረኩ ቁመታቸው በፈቀደላቸው መጠን እያዩ እጃቸው እስኪቃጠል ያጨበጭባሉ፡፡

ሰጥአርጋቸው እግረ መንገዱን አንድ ዘመናዊ ሞባይል በተመስጦ በሚያጨበጭብ ወጣት ኪስ ውስጥ ሲያይ በተለመደው ፍጥነቱ ወስዶ ጓደኞቹን ወደ ቀጠረበት ቦታ ለመድረስ በሰው መሐል ይሹለከለካል፡፡

አሁን እልልታውና ጭብጨባው ጋብ ብሎ ለዕለቱ የሚስማማ ስብከተ ወንጌል እንዲያቀርቡ የተመደቡት ሊቀ ጠበብት መድረኩን ይዘውታል፡፡ 

    “…. ዛሬ እንደሚታወቀው የሁለቱ ዐበይት ሐዋርያት ክብረ በዓል ነው፡፡ ትምህርታችን ግልጥ እንዲሆንልን በወንጌል እጅግ ብዙ ፍሬ ከማፍራታቸው በፊት ስለነበራ    ቸው ሕይወት እናንሣ፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር በተቀመጠ ጊዜ “ጌታ ሆይ ሁሉም ቢክዱ እንኳን፤ እኔ ግን እስከመጨረሻው እከተልሃለሁ” ሲለው በራሱ እጅግ ተመክቶ ነበር፡፡ ነገር ግን መድኃኒታችን ኢየስስ ክርስቶስ “እውነት እውነት እልሃለሁ ዶሮ ሳይጮኸ ሦስት ጊዜ ትክደኛለህ፡፡” አለው፡፡ ጴጥሮስ ተሟገተ፡፡ 

    “ነገር ግን ክርስቲያኖች ታሪኩን እንደምታውቁት የመጀመሪያውን አንዲት ሴትን ፈርቶ ካደ፡፡ እየቀጠለ ሦስት ጊዜ ሲክድ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአይሁድ የመከራ እጅ እንዳለ ዘወር ብሎ ጴጥሮስን አየው፡፡ቅዱስ ጴጥሮስ የክርስቶስ እይታ እንደ መርፌ ወጋው፡፡ ባዶ ትምክህቱ ተገለጸለት፡፡ ከዛ ዘወር አለና አንጀቱ፣ ሆድ ዕቃው እሰኪናወጽ ይንሰቀሰቅ ገባ፡፡ ጌታ እንዳየው ጴጥሮስ ራሱን በራሱ ከሰሰ፡፡ እንባዎቹ እሳት ሆነው በጉንጮቹ ላይ ይጎርፉ ጀመር…” 

የሰጥ አርጋቸው ቡድን አባላት እየቀናቸው ነው፡፡ የአንገት ሀብል፣ የተቀንቀሳቃሽ ስልክ ቀፎ፣ የገንዘብ ቦርሳዎች ሰብስበው ለዳግም ሙከራ ተሰማርተዋል፡፡ 

መምህሩ በተመስጦ ትምህርታቸውን እንደቀጠሉ ነው፡፡ “….ወዳጆቼ እኛንም እኮ በተለያየ ኃጢአት ውስጥ ስንመላለስ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እኛንና ምድርን የፈጠረ አባት የማያየን ይመስለን ይሆን? አንዳንዶቻችን  ፈጣሪ ሰባተኛው ሰማይ ላይ ስለሚኖር፤ ይኼ የምናየው ሰማይ እግዚአብሔርን እንደመጋረጃ የሚጋርደው መሰለን እንዴ?…” እያሉ በሚስብ አንደበታቸው በተመስጦ ይናገራሉ፡፡ 

የሰጥአርጋቸው ጓደኞች እየተመላለሱ የሚያሲዙትን ዕቃ በትልቅ ጥቁር ፌስታል አቅፎ ቁጭ ባለበት ጆሮው የዐውደ ምሕረቱን ትምህርት እያመጣ ያቀብለዋል፡፡ ጆሮ ክዳን የለው፡፡ 

“…. ቅዱስ ጴጥሮስ ግን…..” ቀጥለዋል አባ፤

    “…. በፀፀት እንባው ኃጢአቱን ሁሉ አጠበ፡፡ ትርጉሙ “ሸንበቆ” የነበረ “ስምዖን” የተባለ ስሙን ጌታችን ኢየሱሱ ክርስቶስ ለውጦ ጴጥሮስ አለው፡፡ ጴጥሮስ ማለት “ዐለት” ማለት ነው፡፡እንደገናም ጌታችን ጴጥሮስን ሦስት ጊዜ ደጋግሞ አንድ ጥያቄ ጠየቀው “ጴጥሮስ ትወደኛለህን?” “አዎን ጌታ ሆይ” አለ፤ “ጴጥሮስ ትወደኛለህን” “አዎን ጌታ ሆይ” “ጴጥሮስ ትወደኛለህን” ሲለው ለሦስተኛ ጊዜ ጴጥሮስ አንዲት ኃይለ ቃል ተናገረ “እንድወድህ አንተ ታውቃለህ፡፡” አለው፡፡ በንስሐው ጊዜ ራስን ዝቅ ማድረግን ተምሯልና፡፡ እንደቀደመው ጊዜ በራሱ ትምክህት “እንዲህ አደርጋለሁ፤ እንዲህ እፈጥራለሁ” አላለም፡፡ በኋላም በሕይወቱ ዘመን ሁሉ ባደረገው ክርስቲያናዊ ተግባር ለኢየሱስ ክርስቶስ ያለውን ፍቅር አሳየ የክርስቲያን ጠላቶች ሰቅለው ሊገድሉት በያዙት ጊዜም “እኔ እንደጌታዬ እንዴት እሰቀላለሁ? ራሴን ወደ ምድር ዘቅዝቃችሁ ስቀሉኝ፡፡ በማለት እንደ ዐለት የጠነከረ እምነቱን ገለጸ፡፡ 

የሰባኪ ወንጌሉ ድምፅ ለአፍታ ተገታና መርሐ ግብር መሪው በእልህ መናገር ጀመረ፡፡ “….ምእመናን እባካችሁ ከሌቦች ራሳችሁን ጠብቁ በጣም ብዙ አቤቱታ እየደረሰን ነው፡፡ ሞባይል ስልኮች በሴቶች በኩል ቦርሳቸው በምላጭ እየተቀደደ እየተወሰደ ነው፡፡ ወንዶችም ኪሶቻችሁን ጠብቁ፡፡ በረት የገባው ሁሉ በግ አይደለም!” አለና ይቅርታ ጠይቆ ድምፅ ማጉያውን ለሊቀ ጠበብት ሰጣቸው፡፡ 

ሰጥ አርጋቸው የፕሮግራም መሪውን የእልህ ንግግር እየሰማ ፈገግ ለማለት ሞከረና አንዳች ነገር ሽምቅቅ አደረገው፡፡ ቀና ብሎ ወደ ሰማይ ተመለከተ፡፡ ሰማዩ እንደ ድሮው ነው፡፡ 

ሊቀ ጠበብት የቅዱስ ጳውሎስን ታሪክ ማስተማር ቀጥለዋል፡፡ 

    “ሰማዕቱ ቅዱስ እሰጢፋኖስ ሲወገር ልብሳቸውን ከወጋሪዎቹ ጋር ተስማምቶ ይጠብቅ ነበር፡፡ ሴት ወንዱን እያስያዘ እስር ቤቶችን ሁሉ ሞላ፡፡ በኋላም የጠለቀ ክርስቲያኖችን ለመያዝ እንዲያመቸው የድጋፍ ደብዳቤ ለማምጣት ወደ ደማስቆ ሲሔድ በመንገድ ዳመና ጋረደውና “ሳ..ውል…ሳውል ስለምን ታሳድደኛለህ?” አለው፡፡ በአምላካዊ ድምፅ ጌታ እኮ ሳውልን ማጥፋት ወይም መቅጣት አቅቶት አይደለም፡፡ ምስክር ሲሆነው ምርጥ ዕቃው አድርጎ መርጦታልና፡፡ 

    “ጌታ ሆይ አንተ ማን ነህ?” አለ ቅዱስ ጳዉሎስ ግራ ገብቶት 

    “እኔ አንተ የምታሳድደኝ ኢየሱስ ነኝ አለው፡፡” “ተመልከቱ እንግዲህ” አሉ አባ እጅግ ተመስጠው፡፡ 

አንዳንድ እናቶች ከንፈራቸውን በተመስጦና በሐዘን ሲመጡ ከሚያሰሙት ድምፅ ሌላ ሁሉም በያለበት ቆሞ ጆሮውንና ልቡን ሰጥቷቸዋል፡፡ ሥራ ላይ ከተሰማሩት የሰጥአርጋቸው ቡድኖች በቀር፤ “…. ቅዱስ ጳዉሎስ ኢየሱስ ክርስቶስን እኮ በአካል አላገኘውም፡፡ ታዲያ እንዴት ለምን ታሳድደኛለህ አለው? ክርስቲያን ማለት በክርስቶስ ያመነ ማለት አይደለም ወገኖቼ? አይደለም ወይ?” ሲሉ ከፊት ያሉ ሕፃናት ድምፃቸውን ከሌሎች አጉልተው “ነው!” ብለው መለሱ፡፡ 

    “ሳውልም ያሳድድ የነበረው ክርስቲያኖችን ነበርና ነው፡፡ ዛሬ እኛም ስንቶችን አሳደድን ወገኖቼ! አሁን መርሐ ግብር መሪው የተናገረውን ሰምታችኋል አይደል? እዚህ መድረክ ላይ ብዙ ምእመናን ንብረታቸውን ተገፈው እያለቀሱ ነው፡፡ ማን ነው ከዚህ መሐል በክርስቲያኖች ላይ እጁን የዘረጋው? ዛሬም መድኃኔዓለም “ሳውል ሳውል ስለምን ታሳድደኛለህ? ቅዱስ ጳዉሎስስ የኦሪት ሊቅ ነበርና ማሳደዱ ስለ አምልኮቱ ቀንቶ እንጂ ስለ ሆዱ አልነበረም፡፡ እሱን ሦስት ቀን የዐይኖቹን ብርሃን በመጋረድ የቀጣ አምላክ እኛንማ እንዴት ባለ ጨለማ ይቀጣን ይሆን? እሱን አምነው በተሰበሰቡ ክርስቲያኖች ላይ ደክመው ያፈሩትን በመስረቅ በማታለል ልጆቹን እያሳደድን ነው፡፡ ይኽን ያደረክ ወንድሜ! ይኽን ያረግሽ እኅቴ ሆይ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ለምን ታሳድጅኛለሽ? ይልሻል፣ ይልሃል፡፡…” 

ሲሉ ሰባኪው፤ ሰጥአርጋቸው እጆቹ መንቀጥቀጥ ጀምረዋል፡፡ ሊቀ ጠበብት በሰውኛ ባህርያቸው ሁሉንም እያዩ ያስተምራሉ፡፡ በእሳቸው አካል ላይ ግን ለሰጥአርጋቸው የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ዐይኖች ታዩት፡፡ የተጨነቁ ዐይኖቹን ወደ ሰማይ ላካቸው፡፡ በዚያም የክርስቶስ ዐይን ነበር፡፡ ወደ መሬት አቀረቀረ በዚያም የክርስቶስ ዐይን ነበር፡፡ “ለካ እስከ ዛሬ ክርስቶስ ያየኝ ነበር፤ ያላየሁት እኔ ነኝ” አለ በልቡ፡፡ 

ሊቀጠበብት እንደቀጠሉ ነው “ወገኖቼ የእኛ አምላክ የቀደመውን በደላችንን ሳይሆን የኋላውን ብርታታችንን የሚመለከት ነውና፤ ቅዱስ ጳዉሎስ ጨርቁ እንኳን ድውያንን ይፈውስ ዘንድ እጅግ ብዙ ጸጋ በዛለት፡፡ ሐዋረያው ጳዉሎስም እውነት ለሆነው በፍፁም ፍቅር ሊጠራው ለእኛም ሳይገባው ቁስላችንን ለቆሰለልን፣ እሱ ታሞ ለፈወሰን፣ ተጠምቶ ላረካን፣ ተርቦ ላበላን ለጌታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ሲመሰክር አንገቱን በሰይፍ ተቆረጠ፡፡ ሰማዕትነትን በዚህች ቀን ተቀበለ፡፡ ዛሬ ሐምሌ አምስት ቀን የምናከብረው ቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ጳዉሎስ ሰማዕትነትን የተቀበሉበት ቀን በመሆኑ ነው፡፡ ወገኖቼ እኛስ አንገታችንን የምንሰጠው ለማን ነው? ለዘላለም ሕይወት ለሚሰጠን ለአምላካችን ነው ወይስ በተንኮል ለሚተባበረን ባልንጀራችን? …” 

ሰጥአርጋቸው ጥቁሩን ፌስታል እንደያዘ ድንገት ብድግ አለና በሰዎች መሐል ወደ ፊት ይገሰግስ ጀመር፡፡ አንዱ ባልንጀራው ያገኘውን ይዞ ወደ እሱ ሲመጣ በሰው መሐል ሲሹለከለከ ያየውና “ለእኔ በጠቆመኝ ይሻል ነበር፡፡” እያለ በዐይኑ ይከተለዋል፡፡ የቡድናቸው መሪ ግን ግቡ ቅርብ አይመስልም፡፡ አሁንም በሰዎች መሐል ወደፊት እየተሹለከለከ ነው፡፡ 

ሊቀጠበብት እንደቀጠሉ ነው፡፡ “ቅዱስ ጳዉሎስ አሳዳጅ የነበረ ቢሆንም፤ በኋላ ግን የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱሱ ክርስቶስ ፍቅር በዝቶለት ልሔድ ከእርሱ ጋር ልኖር እናፍቃለሁ..” እያለ በሙሉ ልቡ ይናገር የነበረው ስለ ስሙ ታስሮ ተገርፎ ተሰቃይቶ…” እያሉ ሲናገሩ አንድ ሰውነቱ ሞላ ያለ ወጣት እግራቸው ሥር ተንበርክኮ ከፌስታል ውስጥ ብዙ ቦርሳዎች፣ ተንቀሳቃሽ ስልኮችና ወርቆች ዘረገፈ፡፡ 

ሊቀ ጠበብት ግራ ተጋብተው ወደ ልጁ ተጠጉና “ልጄ ሆይ! ምንድን ነው?” አሉት፡፡

ሰጥአርጋቸው አንገቱ ላይ ያለውን ወርቅ እየፈታ ቀና ብሎ አያቸው፡፡ እሳቸው ዐይን ውስጥ የኢየሱሱ ክርስቶስን ዐይን አየ፡፡ ዐይኖቹ በእንባ ተሞሉና በለሆሳስ “የሚያየኝን አየሁት” አላቸውና እግራቸው ሥር ተደፋ፡፡ 

ሊቀ ጠበብት በርከክ አሉና በፍቅር አቀፉት “ልጄ ስምህ ማነው?” ብለው ጠየቁት፡፡ 

“ሰጥአርጋቸው” አለ አንገታቸው ውስጥ እንደተሸጎጠ፡፡ ሕዝቡ ገና ግራ በመጋባት ማጉረምረም ጀምሯል፡፡ ሊቀ ጠበብት በፍፁም ፍቅር ግንባሩን ሳሙና “እኔስ “ምሕረት” ብዬሀለሁ” አሉት፤ የእጁን የወርቅ ካቴና ሊያወልቅ ሲታገል እያገዙት እግዚአብሔር ይፍታህ ልጄ እግዚአብሔር ይፍታህ ይላሉ፤ ደጋግመው፡፡ 

/ምንጭ፦ ሐመር 17ኛ ዓመት ቁጥር 6/ 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ቅዱስ ተክለ ሃይማኖት

ለአባ የትናንቱ

ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ

ግንቦት 23፣2003ዓ.ም

ያለ ማወቅ ጽልመት ሀገሩን ሲወርሰው ቅዱስ ተክለ ሃይማኖት

ማን ነበር ትውልዱን በወንጌል ያረሰው?

አባ ተክለ ሃይማኖት አባ የትናንቱ

ትዝ አለኝ ተጋድሎው ውል አለኝ ሕይወቱ

በቆላ በደጋ የተንከራተትኸው

የሃይማኖትን ተክል ዞረህ የተከልኸው

የኢትዮጵያ ፀሐይ አባ ተክለ አብ

እስቲ መለስ ብዬ ሥራህን ላስብ

በቀንና በሌሊት ከላይ ታች ዞረህ

ሕዝቡን አዳረስከው አስተምረህ መክረህ

ስንት ነበር አባ ‹የጉዞ አበልህ›?

ያረፍህበት ስፍራ የተዘጋጀልህ

የት ነበር መኝታው ጎን ማሳረፊያህ?

ንገረኝ እባክህ ማን ነበር የሸኘህ?

እሳት አባቴ ሆይ እኔ አመድ ልጅህ

በዘመኔ ቋንቋ እስኪ ልጠይቅህ?

/ምንጭ፦ ሐመር መጽሔት ግንቦት 2003 ዓ.ም እትም/ 

በጎቹና ፍየሎቹ

የ”እናስተውል” 1ኛና መለሰተኛ 2ኛ ደረጃ የሕዝብ ትምህርት ቤት ለስምንተኛ ክፍል ተማሪዎች የተዘጋጀ የመጀመሪያው መንፈቅ ዓመት የአማርኛ ትምህርት ፈተና
በዲ/ን ሄኖክ ኃይሌ
 

ለፈተናው የተሰጠ ሰዓት ፡- 0፡05    
የተማሪው ሙሉ ስም:_________________ ቁጥር:______                            

   

የሚከተለውን ምንባብ በጥንቃቄ አንብቡ
በጎቹና ፍየሎቹ
 
ከዕለታት በአንዱ ቀን በአንድ ሀገር ትልቅ የበጎች በረት ነበረ፡፡ በዚህ የበጎች በረት ውስጥ ብዙ በጎች ይኖሩ ነበር፡፡ ይህ የበጎች በረት ለረዥም ዓመት የቆየ እና ብዙ ታሪክ ያለው በረት ሲሆን በጎቹ ሁሉ ግን የሚኖሩበትን በረት ጥንታዊነት እና ታሪክ በሚገባ የሚያውቁ አይደሉም፡፡ በቅርብ ጊዜ ከሚወለዱት በጎች መካከል ለመስማት ፈቃደኞች ያልሆኑ አሉ እንጂ በረቱን እስከ ዛሬ ድረስ ጠብቆ ለማቆየት ብዙ በጎች ከሚያገሳ አንበሳ ጋር ጭምር ተታግለው ብዙ ድል አድርገዋል፡፡ ብዙ በጎችም ለዚሁ በረት መቆየት ሲሉ አንገታቸውን እስከመስጠት ድረስ ደርሰው ነበር፡፡ ከአሁኑ በጎች ውስጥ ግን አንዳንዶቹ እንኳን ራሳቸውን መሥዋዕት አድርገው ሊሰጡ የቀድሞዎቹ በጎች የፈጸሙትን ገድል እንኳን ለማመን ይከብዳቸዋል ፤ ለመስማትም ይሰለቻሉ፡፡
   
በዚህ በረት ውስጥ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ደግሞ አንድ ችግር ተፈጥሯል፡፡ የችግሩ መነሻ አንዳንድ ፍየሎች በጎች መስለው ከመንጋው መቀላቀላቸው ነው፡፡ እነዚህ ፍየሎች ምንም እንኳን ሥራቸው ፣ ድምፃቸው ፣ አኗኗራቸው ሁሉ ፍየል መሆናቸውን የሚመሰክር ቢሆንም ከበጎቹ በረት ረዥም ጊዜ የቆዩ በመሆናቸው ብዙ በጎችን ግራ ያጋባ ነው፡፡ አንዳንዶቹ አስተዋይና የበግን ጠባይ ከፍየል ለይተው የሚያውቁ በጎች ‹‹ኸረ እነዚህ ፍየሎች ናቸው ፣ ድምፃቸው ፣ አነጋገራቸውና አኗኗራቸው ያስታውቃል!›› እያሉ ሲሟገቱ ከጥቂቶች በቀር የሚሰማቸው አላገኙም፡፡
 
አንዳንዶቹ በጎች ‹‹ምን ችግር አለው ፤ አነጋገራቸው እንደ በግ ባይሆንስ? እስከ መቼ እንደ በግ ብቻ እንናገራለን!›› እያሉ ከመቃወማቸውም በላይ በግ የመሰሉትን ፍየሎች ለመምሰል እነርሱም የፍየሎችን አኗኗር ለመኮረጅ ሞከሩ፡፡ የሚያሳዝነው ግን እውነተኛዎቹ በጎች በግ በመሆናቸው ፍየሎቹን ለመምሰል ያደረጉት ጥረት አልተሳካላቸውም፡፡ ሌሎቹ የዋሃን በጎች ደግሞ ምን ችግር አለው? ‹‹የምንመገበው አንድ ዓይነት ምግብ እስከሆነ ድረስ አንድ እኮ ነን!›› ብለው መከራከር ጀመሩ፡፡ ‹‹ኸረ ከመቼ ወዲህ ነው ፍየሎች አንድ የሆንነው?›› ብለው የተቃወሙ በጎች ደግሞ በእነዚህ በፍየሎች በተታለሉ በጎች ጥርስ ውስጥ ገቡ ‹‹አክራሪ ፣ ጽንፈኛና ወግ አጥባቂ በጎች››  የሚል ስያሜም ወጣላቸው፡፡
 
ይህንን ትርምስ አስቀድሞም ይፈልጉት የነበሩት በግ መሳይ ፍየሎችም ጉዳዩን ማራገብ ጀመሩ፡፡ ‹‹እኛ ለበረታችን ያልሆነው ነገር የለም ፤ እኛ ታማኝ በጎች ነን ፤ ይህቺ በረት ድሮ እንዲህ እንዲህ ነበረች›› ብለው የበረቲቱ መብት ተቆርቋሪዎች ሆኑ፡፡ ይባስ ብለው ድሮ በረቷ የፍየሎች መንጋ እንደነበረች ፣ የምትተዳደረውም በፍየሎች ሕግ እንደነበረ ፤ ከጥቂት ምዕተ ዓመታት ወዲህ በተነሡ በጎች በረቲቱ እንደተበላሸች መወትወት ጀመሩ፡፡ ምንም የማያውቁት በጎች ደነገጡ፡፡ ‹‹ወይኔ በረታችን! ለካ በችግር ላይ ነሽ?›› ብለው በረቲቱን የፍየል በረት ለማድረግ ቆርጠው ተነሡ፡፡ ስለበግነት የሚያነሣን በግ ባገኙት መንገድ ማንቋሸሽም ጀመሩ፡፡
በዚህ መካከል ሌላ ክስተት ተፈጠረ ፤ አንዳንድ ከበጎች ጋር ተቀላቅለው የነበሩ ፍየሎች በይፋ በረቱን ለቅቀው እንደወጡ ተሰማ፡፡ ከወጡ በኋላ ‹‹እውነቱን ተረድተን በግ ከመሆን ፍየል መሆን ይሻላል ብለን ተፀፅተናል ፤ ይህንን እውነት ካወቅን ትንሽ ቆይተናል›› ብለው በአደባባይ ተንሰቅስቀው አለቀሱ፡፡ ሁሉን አይተነዋል ፤ ከእኛ ወዲያ በግነት ለኀሣር አሉ፡፡ በረቱ ውስጥም እያሉ ወሳኝ በጎች እንደነበሩና የበረቱን ጓዳ ጠንቅቀው የሚያውቁ ሊቃውንት እንደሆኑም በዘዴ ጠቆሙ፡፡ አንዳንዶቹም ‹‹የበረቱ ጓዳ›› የሚል መጽሐፍ አዘጋጅተው በተኑ፡፡ ተረባርበው የገዙት በጎቹ ሲሆኑ መልስ ከመስጠት ይልቅ ብዙዎቹ በጎች ተሸማቅቀው ‹‹ጉድ ፣ ጉድ ለካ ይሄ ሁሉ ጉድ አለ?›› ብለው ተንሾካሾኩ፡፡
በዚህ ጊዜ በጎች አሁንም ለሁለት ተከፈሉ፡፡ አስቀድመው ሲቃወሙአቸው የነበሩት በጎች ብዙም ሳይደነቁ ‹‹ከመጀመሪያውስ መች በጎች ነበሩና ነው ፍየል ሆንን የሚሉት ፤ በጎች አለመሆናቸው ይታወቅ ዘንድ ከእኛ ዘንድ ወጡ ፤ በጎች ቢሆኑ ኖሮ ከእኛ ዘንድ ጸንተው በኖሩ ነበር፡፡›› ብለው አስረዱ፡፡ አንዳንድ የዋሃን በጎች ግን ‹‹በግ እገሌ ፍየል ከሆነማ ምን ተረፈን? እንደርሱ ያለ በግ ከየት ይገኛል? ፍየሎችን ያሳፈራቸው እርሱ አልነበረም እንዴ! አይ ይህቺ በረት ምን ቀራት ከእንግዲህ…›› እያሉ ራሳቸውን ነቀነቁ፡፡ ‹‹ከእንግዲህ ትልቅ ነው ብዬ በግ አልከተልም!›› የሚሉም አልጠፉም ይህን ሲሰሙ አስተዋዮቹ በጎች ‹‹አስቀድሞስ በግ በእረኛ እንጂ በግ በበግ ሲመራ የት አይታችኋል ፤ በሉ ይኼ ትምህርት ይሁናችሁ›› አሏቸው፡፡ከዚህ በተጨማሪ “በግ መስለው የሚኖሩ ፍየሎች አሉ” የሚለው የበጎች አቤቱታ አዝማሚያው ያሰጋቸው አንዳንድ በግ መሰል ፍየሎች የበጎችን ልቅሶ ቀምተው ‘ኧረ ፍየሎች በዙ!’ እያሉ ማስመሰል ጀመሩ።
 
ሌላው አሳሳቢ ጉዳይ ደግሞ ትክክለኛው የበጎች በረት የት እንደሆነ ባለማወቅ በጎች ሆነው ሳለ ከፍየሎች መንጋ ጋር የሚንከራተቱ በጎች ጉዳይ ነው፡፡ ወደ ትክክለኛው በረት እንዳይመጡ በበጎቹ በረት አካባቢ የሚታየው ትርምስ የበጎች በረት መሆኑን ስለሸፈነባቸው ተቸገሩ ፣ የብዙዎቹ በጎች ሕይወት ደግሞ የበግ ስለማይመስል የበረቱን በጎ ምስል እንዳይታይ አድርጎታል፡፡ ከፍየል ሌላ የጅብ ፣ የዕባብ ፣ የውሻ ወዘተ ጠባይ የሚያሳዩ በጎች ቁጥር መብዛቱም እነዚህሰ የጠፉ በጎች እንዳይመለሱ እንቅፋት ሆነባቸው፡፡ እረኛው ደግሞ ‹‹ከዚህ በረት ያልሆኑ ሌሎች ብዙ በጎች አሉኝ›› ብሏል፡፡ ከዚህ በረት ውስጥ ያሉ ፍየሎች እንዳሉ ሁሉ ከበረቱ ውጪ ያሉ በጎችም ብዙዎች ናቸው፡፡ ምንም እንኳን እነዚህ የጠፉ በጎች በፍየሎች መካከል ቢሆኑም የበጎች በረት ነገር ሲነሣ ግን በቀላሉ የሚነኩ ፣ልባቸው በቶሎ የሚሰበር ፣ ዕንባ የሚቀድማቸው ናቸው፡፡ የእነዚህ በጎች ጉዳይ እጅግ አሳሳቢ ሆነ፡፡ ‹‹ኸረ ብዙ በጎች እየወጡ ነው!›› እያሉ የሚጮኹም አልታጡም፡፡ አንዳንድ በጎች ደግሞ ለበረቱ የተቆረቆሩ መስሎአቸው ‹‹ይውጡ ፤ ኖረውም አይጠቅሙም! ይላሉ›› እረኛው ግን በጎቹን በበረቱ ለመሰብሰብ ብዙ እንደተሰቃየ ታላላቅ በጎች ታሪክ ጠቅሰው ይናገራሉ፡፡
 
በዚህ ሁሉ መካከል በረቱ እየፈረሰ ነው፡፡ በጎችም እየኮበለሉ ነው፡፡ ፍየሎችም ሌት ተቀን በረቱን የፍየል መንጋ መስፈሪያ ለማድረግ እየተጉ ነው፡፡ ተስፋ የሚጣልባቸው በጎችም ግማሾቹ ወጣ ብለው ሣር ሲግጡ ውኃ ሲጠጡ ፣ ግማሾቹም በዋዛ በተራ እሰጥ አገባ ተጠምደው ፣ ግማሾቹ በፍየሎች ላለመጠመድ ሲሉ የበረቱን ነገር ወደ ጎን ተዉት፡፡ አንዳንዶቹ ደግሞ እንኳን በረቱን ገብተው ሊታደጉ ሌሎች ትንሽ ሲፍጨረጨሩ ሲያዩ ‹‹አዬ የዚህ በረት ነገር በቀላሉ የሚፈታ እንዳይመስላችሁ… ለማንኛውም መፍጨርጨር ጥሩ ነው!›› ‹‹ይኼን ሠራን ብላችሁ ነው? ወይ አለመብሰል!›› ይሏቸው ጀመር፡፡ ነገር ግን በጎቹ ምንም ባያውቁ በበረቱ ማደጋቸው በራሱ ከመብሰል አልፎ ካልተጠቀሙበት ለማረርም የሚበቃ ጊዜ ነበር፡፡ ይሁንና የጥቂቶቹ በጎች ጥረት ውጤቱ ቶሎ እንዳይታይ ደግሞ ምንም እንኳን ፍየሎች ባይሆኑም እንደ በግ ግን መኖር ያቃታቸው ደካሞች በመሆናቸው አቅም አጠራቸው፡፡ በጎችም ሆነው ፍየሎችን እንዴት እናጥቃ በሚለው ጉዳይ መስማማት አቅቷቸው ሥራውን ሳይጀምሩ የጨረሱ ታካቾችም አሉ፡፡ አንዳንድ በጎች መፍትሔ ለማግኘት “ወደ አንበሳ ሔደን አቤት እንበል” ይላሉ። ሌሎች ብጎች ደግሞ ‘አንበሳ ብዙ አንበሳዊ ጉዳዮች አሉበት ደግሞም አንበሳ የሚፈርደው በጎችንና ፍየሎችን በእኩል ዓይን ተመልክቶ ነው ሲሉ ይሞግታሉ።
 
የበረቱ ችግር እየከፋ ፣ የፍየሎቹ አካሔድም እየተስፋፋ ቢመጣም አሁንም ግን ዝምታው ሰፍኗል፡፡ ስለ ፍየሎች ጉዳይ እንዲነሣባቸው የማይፈልጉ በጎችም ተፈጥረዋል፡፡ ‹‹ኸረ ፍየሎች እንዲህ እያደረጉ ነው›› የሚል በግ ሲገኝም ‹‹መዓት አታውራ!›› ተብሎ ይገሠፅ ጀመር፡፡ በዕድሜ የገፉ በጎች ደግሞ ‹‹ይህንን ሳላይ በሞትኩ!›› ብለው ያዝኑ ጀመር፡፡ በእርግጥም በዕድሜ የገፉት በጎች ከመቼውም በላይ የተናቁት አሁን ነው፡፡
 
ፍየሎችን ‹ፍየሎች ናቸው› ብሎ መጥራትም በበጎች ዘንድ ጥላቻን የሚያተርፍ ሆነ፡፡ አንዳንድ በጎች ደግሞ መፍትሔ ያመጡ መስሎአቸው ቢንቀሳቀሱም ፍየልን ፍየል ከማለት ውጪ የበግነትንና የፍየልነትን ልዩነት በሚገባ ማስረዳት ተሳናቸው፡፡ በረቱ የፍየል እንጂ የበግ አልመስል አለ፡፡ አንዳንድ በጎች ጆሮአቸውን ማመን እስኪያቅታቸው የፍየሎች ድምፅ ከበረቱ መሰማቱ እየተለመደ እየተለመደ መጣ፡፡ የሚያስፈራው አዲስ የሚወለዱ ግልገሎች ከልጅነታቸው ጀምሮ ሲሰሙ የሚያድጉት የፍየሎችን ድምፅ በመሆኑ ስለ በግነት እና የበግ ድምፅ ምንም ሳያውቁ የሚያድጉ መሆናቸው ነው፡፡ አንዳንድ በበረቱ ያደጉ በጎች ጭንቀቱን አልቻሉትም፡፡ ‹‹ጆሮዬ ነው ወይስ … እውነት የበረታችን አኗኗር እንደዚህ ነበረ ፤ እውነት ይህቺ በረት ከፍየሎች ጋር አንድ ነበረች? የተሳሳትኩት እኔ ነኝ ወይስ ሌላው?››የሚሉም ነበሩ፡፡ ለማን አቤት እንደሚሉ ጨነቃቸው፡፡ አንዳንዶቹ ደግሞ ለእረኛው አመለከቱ፡፡ በጎ ስላደረጉ በጎች መነገሩ ነውር ሆነ፡፡ ፍየሎቹ ስለ እረኛው ብቻ ነው መነገር ያለበት ባዮች ሆኑ፡፡ ስለ እረኛም ግን ስሙን እየጠሩ ከመፎከር በቀር ፍሬ ያለው ነገር አይወጣቸውም፡፡ በዚህ ከቀጠለ ቀስ በቀስ በግ የመሆንና ፍየል የመሆን ልዩነት ጠፍቶ በረቱ መፍረሱ እንደማይቀር አንዳንድ በጎች ይናገራሉ፡፡ 
 

በምንባቡ መሠረት የሚከተሉትን ጥያቄዎች መልሱ

1.    ለበረቱ መበጥበጥ ምክንያት የሆኑት እነማን ነበሩ?
2.    በግ መስለው የተቀላቀሉት ፍየሎች በምን ይታወቃሉ? (መለያ ጠባያቸው)
3.    አንዳንድ የዋሃን በጎች የተሳሳቱት በምን በምን ነበር?
4.    በግ ነበርን ብለው የወጡት ፍየሎች መውጣት የማያስደንቀው ለምንድን ነው?
5.    ጥሩ ጥሩ በጎች ለምን የበረቱን ችግር ለመፍታት አልቻሉም?
6.    ፍየሎችን ‹ፍየሎች› ብሎ መጥራት ለምን ነውር ሆነ?
7.    ለበረቱ መልካም ነገርን የሚመኙ በጎች ለምን ተባብረው መሥራት አልቻሉም?
8.    ከበረቱ ውጪ ያሉት በጎች ለምን ወደ በረቱ ለመመለስ አልቻሉም?
9.    በጎች መመራት ያለባቸው በሌላ በጎች ነው ወይስ በእረኛ?
10.     የበረቱን ችግር ለመፍታት ምን መደረግ አለበት (ከጓደኞቻችሁ ጋር ተወያዩበት)

ማሳሰቢያ ፡- ተማሪዎች ይህን ፈተና ከተፈተናችሁ በኋላ የበጎቹንና የፍየሎቹን ገጸባሕርያት እያነሣችሁ አንዳችሁ ለአንዳችሁ ስም እየሰጣችሁ እርስ በእርስ እንድትነቃቀፉ አልተፈቀደላችሁም! የጎበዝ ተማሪ መለያ በረቱ ሰላም የሚሆንበትን መፍትሔ መጠቆም ነው፡፡
                                             መልካም ፈተና
ምንጭ፡ሐመር የካቲት 2003 ዓ.ም. 

ነፍስና ሥጋ የውል ስምምነት ተፈራረሙ

በመ/ርት ጸደቀወርቅ አሥራት
ነፍስና ሥጋ እንደከዚህ በፊቱ ለሚጠብቃቸው ከባድ የሥራ ኃላፊነትና አለመግባባት የውል ስምምነት ተፈራረሙ። የውል ስምምነቱን የተፈራረሙት በቀጣዩ ሣምንት የሚገባውን የዐቢይ ፆም ምክንያት በማድረግ ነው።
 
በውሉ ሥነ ሥርዐት ላይ ነፍስ እንደገለጸችው ከዚህ በፊት በአጽዋማት ጊዜ በመካከላቸው የሚፈጠረውን አለመግባባት ለመፍታት ውሉ ጠቃሚነቱ የጎላ ነው።

ባለፉት ዓመታት ሥጋ የአጽዋማትን ወቅት ጠብቆ ነፍስ ተገቢውን ድርሻ እንዳትወጣ እንቅፋት እየሆነ ችግር ሲፈጥር መቆየቱን ገልጸው ስምምነቱ በመካከላችው ሰላም እንዲሰፍን ምክንያት ይሆናል ያሉን በስምምነቱ ሥነ ሥርዐት ላይ የተገኙት የነፍስ አባት ናቸው።

ከፊርማው ሥነ ሥርዐት በኋላ ባነጋገርነው ወቅት ስምምነቱን ተቀብሎ የነፍስን ሥራ ሳይቃወም ሊገዛላት መዘጋጀቱን ሥጋም ቢሆን አልሸሸገም።

በሥነ ሥርዐቱ ላይ የተገኙት ሌሎች ምዕመናንም ሥጋን በቃልህ ያጽናህ እያሉ ከስብሰባው አዳራሽ ሲወጡ እንደተሰሙ “ሪፖርተራችን” ዘግቦልናል።

ትንሣኤ ግዕዝ

 

/ርት ፀደቀ ወርቅ አስራት

የጥንቱ ውበቱ

ጭራሽ ተዘንግቶ፣

ለብዙ ዘመናት

የሚያስታውስ አጥቶ፣

ተዳክሞ ቢያገኙት

ግዕዝ አንቀላፍቶ፣ 

«ሞተ ሞተ» ብለው

አዋጅ አስነገሩ፣

በርቀት እያዩ

ቀርበው ሳያጣሩ፡፡

ታዲያ ይሄን ጊዜ…..

አዋጁን የሰሙት

ቀርበው ወገኖቹ፣

ፍፁም እያነቡ

ግዕዝ….. ግዕዝ ቢሉ

አብዝተው ቢጣሩ፣

በቅፅበት ተነሣ፣

ትንሣኤን አግኝቶ

ለወዳጆቹ ጥሪ

ምላሽ ሊሰጥ ሽቶ፡፡