ከታሪክ አንድ ገጽ

እንደዚህ ሆነ፡፡
በአንዲት መንደር ውስጥ አንድ ሰው ነበረ፡፡ አንደበቱ ከጸሎት እጁ ከምጽዋት ልቡ ከጠዋሐት ተለይቶ የማያውቅ፤ ሰው ተጣላ ማን ያስታርቅ፣ ልጅ አገባ ማን ይመርቅ ቢባል በመጀመሪያ የሚጠራው እርሱ ነው፡፡

ለሽማግሌዎች መኩሪያ ለታዳጊዎች አርአያ መሆንን የሚያነሣ የለም፡፡ ኃጢአትን ሊሠራት ቀርቶ ስሟን ያውቃታል ብሎ የሚገምት የመንደሩ ነዋሪ ከማግኘት አንድ ቀን ሰይጣን ሊመለስ ይችላል ብሎ ተስፋ የሚያደርግ ማግኘት ይቀላል፡፡
ለብዙዎች መለወጥ፣ ለብዙዎች ለጽድቅ መመረጥ፣ ለብዙዎች ከዓለም መመለስ፣ ለብዙዎች ዓለምን ጥሎ መመንኮስ አንድም መሪ ያለያም አበረታች መካሪ እርሱ ነው፡፡
የተናገረው ከልቡና ያስተማረው ከኅሊና ጠብ ሲል ልብ ያደርሳል ኩላሊት ያድሳል፡፡
ያለ ሠርክ ሰዓት እህል የማይቀምስ ያለ ተርታ ነገር ነጠቅ መንጠቅ ያለ የማይለብስ መሆኑን በአካባቢው ሐይቅ ስለሌለ የባሕር ዓሦች ካልሆኑ በቀር የማይመሰክር ፍጥረት አለ ማለቱ ይቸግራል፡፡

ትዳሩን አክባሪ ባለቤቱን አፍቃሪ በመሆኑ ከአብርሃምና ከሣራ ቀጥሎ ለሰርግ ምርቃት እርሱና ባለቤቱ ሳይጠሩ አይውሉም፡፡ አንድ ቀን ከቤተክርስቲያን መልስ ወደ ቤቱ በማምራት ላይ እያለ ዓይኑን ዓይኑ አንድ የማይወራውን ነገር ተመለከተ፡፡ አንድ አገር ያስቸገር መናፍቅ ከርሱ ቤት ግቢ ወጣ፡፡ ለምን?

 
ባለቤቱን አግኝቶ እስኪጠይቃት ነፍሱ የቸኮለችውን ያህል የመኪና እሽቅድድም ተወዳዳሪዎች ቸኩለው አያውቅም፡፡ ገባ፤
‹‹ ይኸ ሰውየ እንዴት መጣ?››
‹‹ ረጋ በልና አስረዳሃለሁ፡፡››
‹‹ ለመናፍቅ ምን እርጋታ ያስፈልገዋል››
‹‹ እኮ ረጋ በል››
‹‹ ለምን ታረሳሽኛለሽ?››
‹‹ ምኑን?›› የሆነ ነገር ብልጭ አለበት፡፡ ሰይጣን እሳት ጫረና ቤንዚን ለቀቀበት፡፡
‹‹ምን ሊሰራ መጣ?››
‹‹ለምን ትቆጣለህ?›› ሰይጣን እሳቱን እፍ በማለት ላይ ነው፡፡
እርስዋ ራስዋ ሰይጣን መስላ ታየችው፡፡ ደክሞታል፡፡ ተናዷል፡፡ ዝሏል፡፡ አእምሮው ዕረፍትን ብቻ ነበር የሚሻው፡፡ ውሳኔ ለመስጠት፤ ነገር ለማመዛዘን ዐቅሙም አልነበረውም፤ ብቻ ሳይሆን ዐቅሙ እንደሌለውም አላወቀም፡፡ አደርጎት የማያውቀውን ዓይኑን አጉረጠረጠና ገፈተራት፡፡ ወደ ኋላ ተንደረደረችና አንገትዋ ኮመዲኖው ጠርዝ ላይ አረፈ፡፡ በስተመጨረሻም መሬት ላይ ተኛች፡፡ ላንዴም ለመጨረሻም፡፡
ነቃ፣ ነቃና አያት፤ ያደረገውን ለማስታወስ ሞከረ፡፡ እርሱ ወይስ ሌላ ሰው? ምንድን ነው የፈጸመው? ሚስቱን ገደላት ማለት ነው? ገዳይ-ወንጀለኛ-ጨዋ-ሰላማዊ-አርአያ-ምሁር- መምህር-ገዳይ-ወንጀለኛ፡፡
ጮኸ – ከማለት ይልቅ የጩኸቱ ደምጽ ፈነዳ ማለቱ ይቀላል፡፡ አካባቢው በሰው ተጥለቀለቀ፡፡
 
እርሱ ያለቅሳል፡፡ ሰውም ያለቅሳል፡፡ አለቃቀሳቸው ግን ለየቅል ነበር፡፡ አንዱ ‹‹ክፉ ተናግራው መልአክ ቀስፏት ነው፡፡ ይላል፡፡ አንዱ ደግሞ ‹‹ የጻድቅ ሰው ዕንባ፡፡ ድሮም የማይናገር ሰው ዕንባው ሰይፉ ነው፡፡›› ሌላው ‹‹ አሁንኮ ወይ እማታለሁ ወይም እገላለሁ ብላ ይሆናል፡፡ ይቺ ሰው መሳይ በሸንጎ የርሱ ደግነት ክፋቷን ሸፍኖላት ዛሬ እግዜር አጋለጣት፡፡›› እርሱ ይገላል ቀርቶ ዝንብ ያባርራል ብሎ የጠረጠረ የለም፡፡ ወንጀሉ ሁሉ የርስዋ ሆነ፡፡
እርሱ ግን የደም ዕንባ አለቀሰ፡፡ የሰዎችን ንግግር በሰማ ቁጥር ዕንባው ይጨምር ነበር፡፡ ‹‹እኔ ነኝ እኔ ነኝ እኔ ነኝ›› አለ ድምፁን ከፍ አድርጎ፡፡
‹‹አይ የዋህ ሰው፡፡ ከባቴ አበሳ አይደል፡፡ ስሟ በክፉ እንዳይነሳ ብሎእኮ ነው›› ይላል አንዱ፡፡
‹‹ስላዘንኩባት ነው ማለቱኮነው›› ቀጠለ ሌላው፡፡ ሊያምነው ቀርቶ ሊሰማው የወደደ የለም፡፡ ሰው የሚናገርለት እና እርሱ የሆነው እየተጋጨበት ኅሊናው ዞረ፡፡ ማን ይመነው፡፡
ለያዥ ለገራዥ ቢያስቸግርም በሽማግሌ ጥረት ሊቀመጥ ቻለ፡፡ ‹‹አይዞህ አንተ አልገደልካት እግዜር መታት እንጂ›› ይሉታል ሽማሎች ሰብሰብ ብሎው፡፡ ያ ለርሱ መርፌ ነው ልብ የሚወጋ፡፡
‹‹እንዲያው እግዚአብሔርን ማመስገን አለብህ፡፡ ፊትህ ላይ ተአምሩን ሲያሳህ›› ሲሉት ደግሞ የተወጋው ልቡ መድማት ጀመረ፡፡
‹‹እኔ አይደለሁም እንዴ አለና መጠራጠር ያዘ፡፡›› አሰበው /ድርጊቱን ሁሉ አሰበው/ ነው እርሱ ነው እኔ ነኝ፡፡ እኔ ነኝ ገዳይዋ- ተንሰቀሰቀ፡፡
‹‹ወይ ግሩም ጻድቃን የወንድማቸው ኃጢአት ከሚገለጥ የራሳቸው ኃጢአት ቢገለጥ የተባለው ደረሰ።›› አሉ አንዲት ወይዘሮ፡፡
‹‹የነ አባ እንጦንስ ታሪክ ሲደገም በዓይናችን አየንኮ›› ሌላዋ ተቀበሉ፡፡
ማን ይመነው፡፡ የልቡን ማን ይወቅ፡፡ እሳት እየከመሩበት መሆኑን ማን ይረዳ፡፡
ጊዜያት ነጎዱ፡፡ ሰው ሁሉ ሊረሳው ጀመረ ጉዳዩን፡፡ እርሱ ግን የሚንተገተግ እሳት ሆኖበታል፡፡
በመጨረሻ እንዲህ ወሰነ፡፡ ለአንድ ለሚወደው ጓደኛው ሊነግረው፡፡ ሐሳብ ቢከፍልልኝ ምክር ቢለግሰኝ ብሎ፡፡
ያደረገውን፡፡ የሆነውን ሁሉ ነገረው፡፡ እየማለ እየተገዘተ የጓደኛው ፊት ሲለዋወጥ ታየው ነጣ- ከዚያ ቀላ መጨረሻ ላይ ጠቆረ፡፡ ‹‹ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ….ለካ አንድ ሰው የለም ባገሩ፡፡ አንተ ስናምንህ ስናከብርህ- ለካ አውሬ ኑረሃል…›› ሰቀጠጠው፡፡ እናም ሸሸው ‹‹ ለኔም ፈራሁህ ››
‹‹እኔኮ የነገርኩህ… ›› አላስጨረሰውም ‹‹ዝም በል!››
ልቡ  ሌላ ነገር ፀነሰ፡፡ የነገርኩት እንዲቀልድብኝ አይደለምኮ አለና ‹‹ባይሆን ነገሩን በልብህ ያዘው›› ሲል ለመነው፡፡
‹‹ገና በአደባባይ ትሰቀላለህ›› ሲል መለሰለት፡፡
ብልጭ አለበት- ሰይጣን እሳት ጫረ፡፡ ዓይኑ ዘወር ዘወር አለ ክትክታ አነሣና ሠነዘረ፡፡ ተጥመልምሎ ወደቀ፡፡ ትኩር  ብሎ ሲያየው ነፍሱ ሸሽታዋለች፡፡ እያለቀሰ፡ ደረቱን እየደቃ ወጣ፡፡ ከቤቱ ብቻ ሳይሆን ከመንደሩ ወጣ፡፡ ወደ በረሃው ሰው ወደ ሌለበት ዘለቀ፡፡ ልክ መንገዱን ሲጨርስ አንድ ሽማግሌ አገኘ፡፡
‹‹ እንደምን ዋሉ አባቴ ››
‹‹እግዚአብሔር ይመስገን ይኼ ደም ምንድነው ልጄ››ልብሱን አሳዩት ደነገጠ፡፡
‹‹እይውልዎት›› አለና ታሪኩን መናገር ሲጀምር ደነገጡና አፈገፈጉ፡፡
‹‹ ዘወር በል አንተ ሰይጣን፡፡!››
‹‹ ይምከሩኝ አባቴ ምን ላድርግ እባክዎ አያውግዙኝ››
‹‹ ዘወር በል ዲያብሎስ እኔንም እንዳትጨምረኝ››
‹‹እኔ እኮ ከቁስሌ ትፈውሰኝ ብዬ እንጂ በቁስሌ ላይ እንጨት የሚሰሰድማ መች አጣሁ፡፡›› አለና ክትክታውን አነሣ እኒያ ሽማግሌ ወደቁ፡፡
ሰው ሁሉ አውሬ መሰለው፡፡ ልቡ እየደነደነ መጣ፡፡ ‹‹ታዲያ ምን ይሁን›› አለው ሰይጤ ‹‹አንተ የመጀመሪያው አይደለህ ››
‹‹ ካሁን በኋላ ማንም ቁስሌን ሊነካ አይችልም ›› አለና በፍጥነት በረሃውን ማቋረጥ ጀመረ፡፡ ማዶ ማዶ ነው አንድ አረጋዊ ካህን ደበሏቸውን ለብሰው ዛፍ ሥር ተቀምጠው ጸሎት ያደርሳሉ፡፡
‹‹ለመጨረሻ ጊዜ›› አለ ‹‹ለርሳቸው ነግሬ መፍትሔ ካልሰጡኝ፤ በቁስሌ ላይ ዘይት መጨመር ትተው ኮምጣጤ ከደፉብኝ የሰው ልጅ ሁሉ ጠላቴ ነው ማለት ነው።›› ወሰነ፡፡
ቀና ብለው አዩት፡፡ ያስፈራል ፡፡ ልብሱ ደም ነክቶታል፡፡
‹‹ ምን ሆንክ ልጄ?›› አሉና ከመቀመጫቸው ተነሡ፡፡ ሠይጣን አንድ ርምጃ አፈገፈገ፡፡
‹‹ ተቀመጥ ደክሞሃል›› ድንጋዩን ለቀቁለት፡፡ ሰይጣን ተናደደ፡፡
‹‹ ምን ሆነሃል?››
በዕንባ ጀምሮ በዕንባ ጨረሰው፡፡
‹‹በተሰቀለው ክርስቶስ ዛሬ ጓደኛ አገኘሁ፡፡›› ዕልል አሉ፡፡
ሰይጣን ፈረጠጠና ዛፍ ሥር ተሸጉጦ ማየት ቀጠለ።
በመገረም ተመለከታቸው፡፡ ‹‹ይገርምሀል፡፡ ሚስቴን ገድዬ፤ ልጆቼን አርጄ፣ የሰው ሀብት ዘርፌ፣ ስንት ልጃገረዶች አባልጌ፣ ሰው መቀመጫ ሲነሳኝ ጻድቅ መስዬ እዚህ ተቀምጫለሁ፡፡ ያንተማ ምን አላት፡፡ በኔ አይነትኮ ያንተ በጥቂት ቀኖና ትሻራለች፡፡››
የፊቱ ጥቁረት ቀነሰ
ክትክታው ከእጁ ወደቀ፡፡
‹‹ በል አሁን ካንድ ሁለት ይሻላል፡፡ ሰው እንደሆነ ቂመኛ ነው ይቅር አይለንም፡፡ እግዚአብሔር ግን መሐሪ ነው፡፡ በዚህ ከቀጠልን እኛ ራሳችን ከሰይጣን መብለጣችን ነው፡፡ ስለዚህ ገደል እንቆፍርና እዚያ ውስጥ ገብተን ንስሐ እንግባ፡፡›› አሉት፡፡ ፈነደቀ፡፡ ዘሎ ተነሣና ዐቀፋቸው፡፡ እናም በዚያው ክትክታ መቆፈር ጀመረ፡፡ እጅግ አድካሚ ሥራ ነው፡፡ አባ ጸሎተ እግዝእትነ ማርያም ይደግማሉ፡፡ ቀና ብሎ አየና እርሱም ጸሎቱን ቀጠለ፡፡
ቀን-ሳምንት-ወር-ሁለት- ሦስት- ወር ፈጀ ቁፋሮው፡፡
ቅጠል ይበላሉ፡፡ አብረው ስለጥንቱ እያወሩ፡፡ ከዚያ ደግሞ ስለ እግዚአብሔር መሐሪነት ያስተምሩታል ዐረፍ ሲሉ፡፡ ይቆዩና ደግሞ ይቆፍራሉ፡፡
በሰው ቁመት ልክ ገደሉ ተቆፈረ፡፡
እንዴት እንግባ፡፡
‹‹አንተ እዚያው ቆየኝ ዕቃውን ሰብስቤ ምግባችንን ይዤ እኔ መጣሁ፡፡›› ተስማማ፡፡
በገመዱ ተንጠልጥለው አባ ወጡ፡፡እላይ ከደረሱ በኋላ ገመዱን ሳቡት፡፡ ደነገጠና ቀና ብሎ አያቸው፡፡
‹‹ ልጄ አሉት አባ›› የነገርኩህ ታሪክ ውሸት ነው፡፡ ‹‹ አንተ እንዳይሰማህ ብዬ ነው ከአሁን በኋላ ምግብህን አመጣልሃለሁ እየሰገድህ፣ እየጾምክ ጸልይ፡፡ እግዚአብሔር ይምራል››  አሉት፡፡ ተናደደ ክትክታው አጠገቡ የለም፡፡ ከግራ ገደል ከቀኝ ገደል አለቀሰ፡፡ አነባ፡፡
‹‹ዕንባ የኃጢአት ክምር ትንዳለች ›› አሉ አባ፡፡
ምንም አማራጭ የለም፡፡ ጸሎቱን ጀመረ፡፡
አባም በዘጠኝ ሰዓት ምግቡን አስበው ያመጡ ነበር፡፡
ከሰባት ዓመት በኋላ አባ ምግቡን ሊያደርሱለት ሲሄዱ ክንፍ አውጥቶ ሲበር አዩት፡፡
 
ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፦  ሐመር 7ኛ ዓመት ቁጥር 3 ሰኔ/ሐምሌ 1991 ዓ.ም.

በሕይወት ያለ ማስታወሻ ለገና ሥጦታ

የዘመነ ማቴዎስ 4ኛ ወር የመጨረሻውን ቀን በሚመስጥ የሕይወት ትምህርት በመማር አሳለፍኩት፡፡ ጠዋት ከጓደኛዬ ጋር ቁርስ አድርገን እርሱ ሊወስደኝ ካሰበው ሥጦታ መስጫ ቦታ ሄድን፡፡ይህ የስጦታ መለዋወጫ ቦታ ለእነርሱ ልማድ ነው፡፡ በዓል በመጣ ቁጥር የሚሄድበት የውዴታ ግዴታ የሆነበት ልማድ በእርግጥ ሲጀምረው ጥልቅ ደስታና እርካታ የተሞላ ነበር።

እኔ ከጉዟችን መልስ በድርጊቱ ተደምሜያለሁ፣ እርሱ በዓመት ሦስቴ ለበዓላት በመሄድ ገንዘብ ያደረገው ልማድ!! ይህ የልደት በዓል በጠዋቱ መልካም የሕይወት ተሞክሮ እያስተማረኝ እንደሆነ መረዳቴ የዘመኑን መልካም ጅማሮ እንድወደው አስገደደኝ ገና ሦስት ሩብ ዓመታት ይቀራሉና!!

‹ታምሜ ጠይቃችሁኛል?…… ተርቤ አብልታችሁኛል?› የሚሉት የክርስቶስ የወንጌል ቃላት ለእርሱ የሕይወት ልምምድ መሠረቶች ነበሩ፡፡ እንዴት ልፈጽመው ከሚል በጎ መሻት የመነጨ ልምድ፣ እናም ወሮታ የማይከፈልበት ብድር ከማይመለስበት፣ ይሉኝታ ከሌለበት፣ ከሥጋዊ የራስ ጥቅም አድልዎ የነጻ ዕረፍት፣ ጥልቅ ደስታና የሕይወት እርካታ ያገኝ ዘንድ በበዓላት በሆስፒታል የተኙ ህመምተኞችን ቤት ያፈራውን በመያዝ ‹እንኳን አደረሳችሁ…..እግዚአብሔር ከእናንተ ጋር ይሁን፤ እግዚአብሔር ይማራችሁ! በማለት ይጠይቃቸዋል፡፡ ከቤተሐኪም ገብቶ የሚጠይቃቸው፣ የሚያጫውታቸውና የሚያጐርሳቸው በአጠገባቸው አስታማሚ(ጠያቂ) የሌላቸውን ብቸኛ ህመምተኞች ናቸው፡፡ ይደርስላቸዋል፣ ከጐናቸው!!

አዎ! ማንም ህመምተኛ ድኖ ሲነሣ ውለታ ለመክፈል አይጨነቅም በውለታ አልታሰረምና፡፡ አያውቃቸውም አያውቁትም ቀድሞ እንዲሁ ነበር ዛሬም እንደዛው ወደፊትም እንዲያው ሊሆን ይችላል፡፡ እናም የማያውቁትን በመጠየቃቸው ብድር የማይመልሱትን እርሱም ለነገ ብድራት የማያስቀምጠውን ግን ህመምተኛ ጠያቂን ፈላጊ የሆነን ሰው እንደው ደርሶ ‹እንኳን አደረሰህ› ብሎ የፈጣሪን ምሕረት ለምኖ መጽናናትን መፍጠር እርግጥ ምን ያህል ዋጋ ያለው ደስታ ይኖረው ይሆን… ወዘተርፈ፡፡

የዓውደ ዓመት በዓል ይሄን ያህል ደስታ ይፈጥር ይሆንን? እርግጥ በቤተሰብ መሀል ለሚኖር ሰው ደስታው፣ ጨዋታው፣ ሁካታው፣ መጠያየቁ፣ መልካም ምኞቱ ደስታ ሊፈጥሩ ይተጋገዙለት ይሆናል ይሄን ቢጨምርበት ግን ደስታው ሊያገኘው ከሚታገለው እጥፍ ሲበዛለት ሲበረክትለት ወደ እርካታ ሲመራው በሕይወቱ ሊማር እንደሚችል አምናለሁ፡፡ ምናልባትም የምንጠይቀው አንዱ ህመምተኛ የሕይወትን ቃል ሊያሰማን ምክንያት ቢሆንስ? ኑ እንውረድ በዓርአያችን እንደምሳሌያችን ሰውን እንፍጠር ያለው ለዚህ ይሆን እንዴ?!
ይህ ነው የገና ሥጦታ የተሰጠኝ፣ የሕይወት ትምህርታዊ ገጸ በረከት! ማስተዋሉን ላደለው መልካም ትምህርት ነበር ግሩም!!

/ በዕለት ውሎ መመዝገቢዬ ለጽሑፍ በሚሆን መልክ የተቀዳ
በኤርምያስ ትዕዛዝ  ዘሐብታም
መስከረም 1 2001 ዓ.ም /

ይህን ያውቁ ኖሯል?

የመነኮሳት ሕይወት

ምንም እንኳን የድንግልናና የምናኔ ኑሮ ቀደም ብሎ የተጀመረ ቢሆንም የምንኩስና መሥራችና አባት ቅዱስ እንጦንስ ነው፡፡ አባ እንጦንስ ግብፅ ውስጥ በምትገኝ ቆማ በምትባል ቦታ በ251 ዓ.ም ተወለደ፡፡ ወላጆቹ ሀብታሞችና ደጋግ ሰዎች ነበሩ፡፡ ከወላጆቹ ዕረፍት በኋላ የነበረውን ሀብት ለድሆች መጽውቶ መንኩሶ ብዙ ዓመት በብሕትውና ኖረ፡፡

በዚያን ጊዜ ብዙ ታምራትን ስለሠራ ሕዝቡ ግማሹ እሱን አይቶ ለማድነቅ የቀረው ደግሞ በእርሱ ጸሎት ለመፈወስ ወደነበረበት ቦታ ይጐርፍ ነበር፡፡ እርሱም በ356 ዓ.ም ዐረፈ፡፡

አባ ጳኩሚስ የተባለ ሌላው አባት በላይኛው ግብፅ ውስጥ ብዙ ገዳማትን በመሥራት የምንኩስናን ሕግና ሥርዓት በመወሰን ስለምንኩስና መስፋፋት ብዙ ደክሟል /290-347 ዓ.ም/፡፡ አንድ ቀን ወደ ዱር እንጨት ፍለጋ ሔዶ ሳለ የእግዚአብሔር መልአክ ተገለጸለትና እንደ አባቶቻችን ሐዋርያት የአንድነትን ማኅበር ለመሥራት መነኮሳትን እንዲሰበስብ አዘዘው፡፡ ብዙ አማኞች እየናፈቁት ማግኘት ያልቻሉትን ገዳማዊ ሕይወት ያገኙ ዘንድ ገዳም ለመመሥረት የሚስችለውንና የሚያስተዳድርበትን በነሐስ ላይ የተቀረጸ ሕግ ሰጠው፡፡ አባ ጳኩሚስም ከመልአኩ በተሰጠው ሕግ መሠረት የሚተዳደር ገዳም አቋቋመ፡፡ ይኸውም መነኮሳቱ ጠዋትና ማታ አብረው እንዲፀልዩ በአንድነት እንዲሠሩ ገቢና ወጪያቸው አንድ ላይ እንዲሆን በአንድነት እንዲመገቡ፣ ልብሳቸው አንድ አይነት እንዲሆንና እነዚህን የመሳሰሉትን ደንቦች አወጣላቸው፡፡ በዚህ መሠረት መነኮሳቱ የዕለት ምግባቸውን የሚያገኙት እየሠሩ ነበር፡፡ ከሴቶችም የምንኩስናን ሕይወት የጀመረች የአባ ጳኩሚስ እህት ማርያም ናት፡፡

ከዚህ በኋላ በ4ኛው መቶ ክ/ዘመን ጀምሮ ምንኩስና በግሪክ፣ በሮም፣ በሶሪያና በሌሎችም ሀገሮችም እየተስፋፋ ሄደ፡፡

የምንኩስናን ሕይወት ወደ ኢትዮጵያ ያመጡ በ5ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በጉባዔ ኬልቄዶን /በሃይማኖት ስደት/ ምክንያት ከቁስጥንጥንያ፣ ከግብፅ፣ ከሶርያ፣ ከሮም፣ ከአንጾኪያ ወደ ኢትዮጵያ የመጡ ዘጠኙ ቅዱሳን መነኮሳት ናቸው፡፡ ምንኩስና ከተመሠረተ ጀምሮ በየጊዜው ሕዝቡ ታላላቆችም ሳይቀሩ ወደ ገዳማቱ እየሄዱ ይመነኩሱ ነበር፡፡

ነገር ግን ከ9ኛው መቶ ዘመን ጀምሮ በማኅበር ከሚኖሩት መነኮሳት መካከል ጥቂቶቹ ቀስ በቀስ ለብቻ በተለየ ቤት መኖር እያንዳንዱ መነኩሴ ለብቻ በፈለገበት ጊዜ መብላትና መተኛት ስለጀመረ በየገዳማቱ የመነኮሳቱ ኑሮ በማኅበር የሚኖሩትና ለብቻቸው የሚኖሩት ለሁለት ተከፈሉ፡፡

የድንግልና መሠረቱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ «ስለ መንግሥተ ሰማያት ሰውነታቸውን ጃንደረባ ያደረጉ አሉና፤ መፈጸም የሚችል ግን ይፈጽም» ሲል የተናገረው የሕግ ቃል ነው፡፡ ማቴ. 19፡12

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

/ምንጭ፦ ‘የዛሬዋ ኢትዮጵያ በመጽሐፍ ቅዱስ’ በዲ/ን አሐዱ አስረስ፣ ነሐሴ 1992 ዓ.ም/