“የጌታን ቤት በወርቅ ወይም በብር ባለማስጌጣቸው ከጌታ ዘንድ በሰዎች ላይ የሚመጣ አንዳች ቅጣት የለም”
ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በማቴ.14፥23 ያለውን ንባብ በተረጎመበት ድርሳኑ ከሰው የሚቀርብላቸው ከንቱ ውዳሴን ሽተው ሕንፃ ቤተ ክርስቲያንን ሲያስጌጡ የሚታዩ ነገር ግን እንደ አልዓዛር ከደጃቸው የወደቀውን ተርቦና ታርዞ አልባሽና አጉራሽ ሽቶ ያለውን ደሃ ገላምጠው የሚያልፉትን ሰዎች ይገሥፃል፡፡ በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ዘመን አንዳንድ ባለጠጎች ደሃ ወገናቸውን ዘንግተው ከእግዚአብሔር ዋጋ የሚያገኙ መስሎአቸው ቤተ ክርስቲያንን የወርቅና የብር ማከማቻና መመስገኛቸው አድርገዋት ነበር፡፡ ይህ ጥፋት በአሁኑ ጊዜ መልኩን ቀይሮ በሕንፃ ኮሚቴ ሰበብ ምዕመኑን ዘርፎ የራሳን ሀብት ማከማቸት በአደባባይ የሚሰማና የሚታይ ምሥጢር እየሆነ ነው፡፡ እነዚህን በዮሐንስ አፈወርቅ ዘመን ከተነሡት ጋር ስናነጻጽራቸው እነዚያ ከእነዚህ በጣም ተሸለው እናገኛቸዋል፡፡ ነገር ግን ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እነዚያን እንዴት ብሎ እንደሚወቅሳቸው እንመልከትና በዚህ ዘመን የሚፈጸመው ዐይን ያወጣ ዘረፋ ምን ያህል አስከፊ ቅጣትን ሊያመጣ እንደሚችል እናስተውለው፡፡
… ሰው ወላጆቻቸውን በሞት ያጡ ሕፃናትንንና ረዳት ያጡ ባልቴቶችን ከልብስ አራቁቶ በወርቅ የተለበጠ ጽዋ ለቤተ ክርስቲያን በማበርከቱ ብቻ የሚድን እንዳይመስለው ይጠንቀቅ፡፡ የጌታን ማዕድ ማክበር ከፈለግህ ስለእርሷ የተሠዋላትን ነፍስህን ከወርቅ ይልቅ ንጹሕ በማድረግ በእርሱ ፊት መባዕ አድርገህ አቅርባት፡፡ ነፍስህ በኃጢአት ረክሳና ጎስቁላ አንተ ለእርሱ የወርቅ ጽዋ በማግባትህ አንዳች የምታገኘው በረከት ያለ አይምሰልህ፡፡ ስለዚህም በወርቅ የተሠሩ ንዋያተ ቅድሳትን መስጠት የእኛ ተቀዳሚ ተግባር አይሁን፡፡ ነገር ግን የምናደርገውን ሁሉ በቅንነት እናድርግ እንዲህ ከሆነ ከእግዚአብሔር የምናገኘው ዋጋ ታላቅ ይሆንልናል፡፡ ሥራችንን በቅንነት መሥራታችን ከወርቅ ይልቅ እጅግ የከበረ ዋጋ አለው፤ እንዲህ በማድረጋችንም ከቅጣት እናመልጣለን፡፡