ዕለተ ዓርብ በሰሙነ ሕማማት
ዕለተ ዓርብ አዳምን ከሰይጣን ባርነት ነፃ ለማውጣትና የእርሱን የበደል ዕዳ ለመክፈል አምላካችን መከራ መስቀሉን የተሸከመበት ዕለት፣ የኀዘን ዕለት፣ የድኅነትም ዕለት ነው፡፡ ዓርብ ማለት ዐረበ ገባ (ተካተተ) ካለው የግእዝ ግስ የተገኘ ሲሆን ትርጕሙም መካተቻ ማለት ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ፍጥረቱን ከእሑድ ጀምሮ በስድስተኛው ቀን ዓርብ አዳምን በመፍጠር ሥራውን ሁሉ አጠናቋልና (አካቷልና)፡፡ በኋላም በኦሪት ሕዝበ እስራኤል ከሰማይ የሚወርድላቸውን መና በሙሴ ትእዛዝ መሠረት ዓርብ ዕለት የቅዳሜን ጨምረው (ቅዳሜ ሰንበት ስለሆነ እህል መሰብሰብ ስለማይገባ) አካተው ይሰበስቡ ነበር፡፡ (ዘፀ.፲፮፥፬)