‹‹ተቈጡ፤ አትበድሉም›› (ኤፌ. ፬፥፳፮)
ቊጣ ተገቢ እንደሆነ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለኤፌሶን ሰዎች በጻፈው መልእክቱ ‹‹ተቈጡ፤ አትበድሉም፤ ፀሐይ ሳይጠልቅም ቊጣችሁን አብርዱ›› በማለት ተናግሯል፡፡ ከሰዎች ጋር በሚኖረን ግንኙነት ውስጥ እውነት ሲጠፋ ወይንም ሐሰት ሲንሰራፋ ኃጢአትን በመንቀፍ መቈጣታችን ተገቢ ነው፡፡ ሰዎችን ከስሕተት እና ጥፋት ለመመለስ መቈጣት የተፈቀደ እንደሆነ በዚሁ እንረዳለን፡፡ ሆኖም ግን ከልክ ባለፈ ቊጣ የሰዎችን ስሜት በመጕዳት መበደል ኃጢአት ነው፡፡ ይህም ማለት ትክክል ያልሆነን ነገር ስንመለከትና ስንሰማ ወይንም ስሕተት ሲፈጸም አይተንና ሰምተን ብንቈጣ ተገቢ ሆኖ ሳለ የመቈጣታችን ስሜት ግን ለመፍትሔ እንጂ ለባሰ ጥፋት የሚዳርግ ከሆነ እንዲሁም የተቈጣንበት ነገር አግባብነት ከሌለው የማይገባ ቊጣ እንደሆነ መረዳት ይኖርብናል፤ የሚገባ ቊጣ ሲሆን ግን ትክክል መሆኑን በዚሁ መረዳት ያስፈልጋል፡፡ (ኤፌ. ፬፥፳፮)