ዘመነ ክረምት ክፍል ሁለት

ነሐሴ ፱ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

የተወደዳችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች! በክፍል አንድ ዝግጅታችን የመጀመሪያው የዘመነ ክረምት ክፍለ ጊዜ (ከሰኔ ፳፭ እስከ ሐምሌ ፲፰ ቀን ድረስ ያለው) ዘርዕ፣ ደመና እንደሚባል በማስታዎስ ይህ ወቅት ደመና ሰማዩን የሚሸፍንበት፤ የዝናም መጠን የሚያይልበትና መሬት በዝናም ረክታ ዘር የምታበቅልበት ጊዜ እንደኾነ ጠቅሰን የወቅቱን ኹኔታ ከሕይወታችን ጋር በማዛመድ ለመዳሰስ ሞክረን ነበር፡፡ በዛሬው ዝግጅታችን ሁለተኛውን የዘመነ ክረምት ክፍለ ጊዜ የሚመለከት ትምህርት ይዘን የቀረብን ሲኾን በወቅቱ ባለማስነበባችን ይቅርታ እየጠየቅን ጽፋችንን እነሆ!

ከሐምሌ ፲፱ እስከ ነሐሴ ፲ ቀን ድረስ ያለው ሁለተኛው ክፍለ ክረምት ‹‹መብረቅ፣ ነጎድጓድ፣ ባሕር፣ አፍላግ፣ ጠል›› በመባል የሚታወቅ ሲኾን፣ ይኸውም የመብረቅና የነጎድጓድ ድምፅ በብዛት የሚሰማበት፤ የባሕርና የወንዞች ሙላት የሚያይልበት፤ የምድር ልምላሜ የሚጨምርበት ወቅት ነው፡፡ በዚህ ክፍለ ጊዜ ውስጥ በሚገኙ ዕለታት በቤተ ክርስቲያን በማኅሌቱ፣ በሰዓታቱ፣ በቅዳሴው የሚነገረው ቃለ እግዚአብሔር ይህንን ኹሉ ሕገ ተፈጥሮ የሚዳስስና የእግዚአብሔርን አምላካዊ ጥበብ የሚያስረዳ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ነው፡፡

መብረቅ እና ነጎድጓድ

ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ ‹‹ወገብረ መብረቀ ለጊዜ ዝናም፤ መብረቅን ለዝናም ምልክት አደረገ፤›› በማለት እንደ ገለጸው መብረቅ በዝናም ጊዜ የሚገኝ ፍጥረት ሲኾን የሚፈጠረውም ውሃ በደመና ተቋጥሮ ወደ ላይ ከተወሰደ በኋላ በነፋስ ኃይል ወደ ምድር ሲወርድ በደመና እና በደመና መካከል በሚከሠት ግጭት አማካይነት ነው፡፡ ይህንን የመብረቅ አፈጣጠርም ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን በቅቤና በዐረቄ አወጣጥ ይመስሉታል፡፡

ወተት ሲገፋ ቅቤ እንደሚወጣ፤ ልዩ ልዩ የእህል ዝርያ ከውሃ ጋር ኾኖ በእሳት ሲሞቅ ዐረቄ እንደሚገኝ ኹሉ ደመና እና ደመና ሲጋጩም መብረቅ ይፈጠራልና:: የምድር ጠቢባንም ሞቃት እና ቀዝቃዛ አየር ሲጋጩ መብረቅ እንደሚፈጠር ይናገራሉ፡፡ ከዚህ ላይ ዘመናዊው ትምህርት ከመምጣቱ በፊት መጽሐፍ ቅዱስ ስለ መብረቅ አፈጣጠር አስቀድሞ ማስተማሩን ልብ ይሏል /መዝሙረ ዳዊት አንድምታ ትርጓሜ፣ መዝ.፻፴፬፥፯/፡፡ ነጎድጓድ ደግሞ መብረቅ በሚፈጠርበት ጊዜ የሚሰማው አስፈሪ ድምፅ ነው /ራእ.፬፥፭/::

መብረቅና ነጎድጓድ በእግዚአብሔር መቅሠፍት እና በቃለ እግዚአብሔር (በቍጣው) ይመሰላሉ፡፡ መብረቅ ብልጭታውና ድምፁ (ነጎድጓዱ) እንደሚያስደነግጥና እንደሚስፈራ ኹሉ እግዚአብሔርም መቅሠፍት ሲልክና ሲቈጣ የሰው ልጅ ይጨነቃል፤ ይረበሻልና፡፡ ‹‹ቃለ ነጎድጓድከ በሠረገላት አስተርአየ መባርቅቲሁ ለዓለም ርዕደት ወአድለቅለቀት ምድር፤ የነጐድጓድህ ድምፅ በዐውሎ ነበረ፡፡ መብረቆች ለዓለም አበሩ፤ ምድር ተናወጠች፤ ተንቀጠቀጠችም፤›› እንዳለ ቅዱስ ዳዊት /መዝ.፸፮፥፲፰/፡፡ ይህም ግብጻውያን እስራኤላውያንን ከባርነት ባለመልቀቃቸው የደረሰባቸውን ልዩ ልዩ መቅሠፍትና መዓት የሚመለክት ምሥጢር ይዟል:፡

እንደዚሁም እስራኤላውያን የኤርትራን ባሕር በተሻገሩ ጊዜ ‹‹ንሴብሖ ለእግዚአብሔር ስቡሐ ዘተሰብሐ›› እያሉ ለእግዚአብሔር ምስጋና ማቅረባቸውን ያመለክታል፡፡ በተጨማሪም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተጠመቀ ጊዜ እግዚአብሔር አብ ከላይ ከሰማይ ኾኖ ‹‹የምወደውና የማፈቅረው ልጄ ይህ ነው፤ እርሱንም ስሙት፤›› በማለት መናገሩንና ወንጌለ መንግሥተ ሰማያት (ቃለ እግዚአብሔር) በቅዱሳን ሐዋርያት፣ በሰብዓ አርድእት፣ በአበው ሊቃውንት አማካይነት በመላው ዓለም መሰበኩን ያጠይቃል /ትርጓሜ መዝሙረ ዳዊት/:፡

እንደ ሌሎቹ ፍጥረታት ኹሉ መብረቅና ነጎድጓድም አስገኛቸውን፤ ፈጣያቸውን ልዑል እግዚአብሔርን ያመሰግኑታል፡፡ ሊቁ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫም ይህንን ሥርዓት ‹‹… ዘበጸዐዕ ይትነከር ወእመባርቅት ይትአኰት ወይትናበብ በእሳት ድምፀ ነጎድጓዱ በሠረገላት፤ በብልጭታ የሚደነቅ፤ በመብረቆች የሚመሰገን፤ በእሳት ውስጥ የሚናገር፤ የነጎድጓዱም ድምፅ በሠረገሎች ላይ የኾነ እግዚአብሔር ንጹሕ፣ ልዩ፣ ክቡር፣ ጽኑዕ ነው፤›› ሲል ገልጾታል /መጽሐፈ ሰዓታት/::

ቅዱስ ዳዊትም በመዝሙሩ ‹‹ይሴብሕዎ ሰማያት ወምድር ባሕርኒ ወኵሉ ዘይትሐወስ ውስቴታ፤ ሰማይና ምድር ባሕርም በእርስዋም የሚንቀሳቀስ ሁሉ ያመሰግኑታል፤›› በማለት ሰማዩም፣ ምድሩም፣ ባሕሩም፣ ወንዙም እግዚአብሔርን እንደሚያመሰግን ተናግሯል /መዝ.፷፰፥፴፬/፡፡ ይህም እግዚአብሔር በመላእክትም፣ በሰው ልጅም፣ አንድም በትሑታኑም በልዑላኑም፤ በከተማውም በገጠሩም እንደዚሁም በባሕር ውስጥ በሚመላለሱ ፍጥረታት ኹሉ የሚመሰገን አምላክ መኾኑን ያስረዳል፡፡ የማይሰሙ፣ የማይናገሩ፣ የማያዩ ግዑዛን ፍጥረታት እንዲህ እግዚአብሔርን የሚያመሰግኑ ከኾነ በእርሱ አርአያና አምሳል የተፈጠረው፤ ሕያዊት፣ ለባዊትና ነባቢት ነፍስ ያለችው የሰው ልጅማ ፈጣሪውን እንዴት አልቆ ማመስገን ይገባው ይኾን?

ከዚሁ ኹሉ ጋርም ደመና እና ደመና ተጋጭተው መብረቅን እንደሚፈጥሩ ኹሉ የሰው ልጅ ባሕርያተ ሥጋም እርስበርስ ሲጋጩና አልስማማ ሲሉ በሰው ልጅ ስሜት ቍጣ፣ ብስጭት፣ ቅንዓት፣ ወዘተ. የመሳሰሉ የጠባይዕ ለውጦች ይከሠቱና ኀጢአት ለመሥራት ምክንያት ይኾኑበታል፡፡ ‹‹ከልብ ክፉ ዐሳብ፣ መግደል፣ ምንዝርነት፣ ዝሙት፣ መስረቅ፣ በውሸት መመስከር፣ ስድብ ይወጣል፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ /ማቴ.፲፭፥፲፱/፡፡ የመብረቅና የነጎድጓድ ድምፅ እንደሚያስፈራው ኹሉ እነዚህ በሥጋዊ ባሕርይ አለመስማማት የሚፈጠሩ የኀጢአት ዘሮችም ፍርሃትንና መታወክን በሰው አእምሮ ውስጥ እንዲመላለስ ያደርጋሉ፤ ከኹሉም በላይ በምድርም በሰማይም ቅጣትን ያስከትላሉ:: ለዚህም ነው ጠቢቡ ሰሎሞን ‹‹ኀጥእ ማንም ሳያሳድደው ይሸሻል፤ ጻድቅ ግን እንደ አንበሳ ያለ ፍርሃት ይኖራል፤›› ሲል የተናገረው /ምሳ.፳፰፥፩/፡፡

እንግዲህ የሰው ልጅ ራሱን ከክፉ ዐሳብና ምኞት በመጠበቅ አእምሮዉን ለመልካም አስተሳሰብና አመለካከት፤ ለክርስቲያናዊ ምግባር ቢያስገዛ በምድር በሰላምና በጸጥታ ለመኖር፤ በሰማይም መንግሥቱን ለመውረስ እንደሚቻለው በመረዳት ባሕርያተ ሥጋችን ተስማምተውልን በጽድቅ ሥራ እንድንኖር እግዚአብሔርን በጸሎት መጠየቅ ይኖርብናል::

ባሕር እና አፍላግ

ባሕርና አፍላግ በቃልና በመጠን፣ ወይም በአቀማመጥ ይለያዩ እንጂ ሁለቱም የውሃ ክፍሎች ናቸው፡፡ ‹‹ባሕር›› አንድም ብዙም ቍጥርን የሚወክል ግእዝ ቃል ሲኾን ይኸውም በጎድጓዳ መልክዐ ምድር ውስጥ የሚጠራቀም ጥልቅ የኾነ የውሃ ክምችት ማለት ነው /ዘፍ.፩፥፲/፡፡ ‹‹አፍላግ›› የሚለው የግእዝ ቃልም የ‹‹ፈለግ›› ብዙ ቍጥር ኾኖ ትርጉሙም ወንዞች ማለት ነው፡፡ ይህም ከውቅያኖስ፣ ከባሕር ወይም ከከርሠ ምድር መንጭቶ ረጅም ርቀት የሚፈስ የውሃ ጅረትን አመላካች ነው /ዘፍ.፪፥፲፤ መዝ.፵፭፥፬/፡፡ በዚህ ወቅት የባሕርና የወንዞች መጠን ለዋናተኞች፣ ለመርከብና ለጀልባ እንቅስቃሴ አስቸጋሪ እስኪኾን ድረስ ከቀድሞው በበለጠ መልኩ በሙላትና በኃይል ይበረታል፤ ከሙላቱ የተነሣም ሰውን፣ ንብረትን እስከ ማስጠም እና መውሰድ ይደርሳል::

ይህ የባሕርና የወንዞች ሙላትም የምድራዊ ሕይወት መከራና ፈተና፣ ሥቃይና ፈቃደ ሥጋ (ኀጢአት) ማየልን፤ ዳግመኛም በሰው ልጅ ኀጢአት ምክንያት የሚመጣ ሰማያዊም ኾነ ምድራዊ ቅጣትን ያመለክታል፡፡ እንደዚሁም የእግዚአብሔርን የተአምራት ብዛት ይገልጻል፡፡ ‹‹ወዓሠርከኒ ውስተ ማይ ብዙኅ ወኢይትዐወቅ ዓሠርከ፤ መንገድህ በባህር ውስጥ ነው፤ ፍለጋህም በብዙ ውኆች ነው፤›› እንዲል /መዝ.፸፮፥፲፱/፡፡ ይኸውም የእግዚአብሔር መንፈስ በመላው ዓለም ሰፍኖ እንደሚኖርና በሃይማኖት፣ በምግባር ጸንተው፣ ከኀጢአት ተለይተው እርሱን የሚሹ ኹሉ ይቅርታውን እንደ ውኃ በቀላሉ እንደሚያገኙት የሚያስረዳ ምሥጢር አለው፡፡ የኀጢአት ባሕር እንዳያሰጥመን፤ የኀጢአት ወንዝ እንዳይወስደን ኹላችንም ራሳችንን ከፈቃደ ሥጋ (ከስሜታዊነት) ተጠብቀን መንግሥቱን እንወርስ ዘንድ አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር በቸርነቱ ይርዳን፡

ጠል

‹‹ጠል›› የሚለው ቃል ‹‹ጠለ – ለመለመ›› ከሚል የግእዝ ግስ የወጣ ሲኾን ትርጕሙም ‹‹ልምላሜ›› ማለት ነው፡፡ ዘመነ ክረምት ከጀመረበት ጊዜ ጀምሮ ልምላሜ ቢኖርም በስፋት የሚነገረው ግን ከሐምሌ ፲፱ ቀን እስከ ነሐሴ ፲ ባለው ጊዜ ውስጥ ነው፡፡ ይህ ወቅት የሚበሉትም የማይበሉትም አብዛኞቹ ዕፀዋት በቅለው ለምልመው የሚታዩበት ጊዜ ነው፡፡ ጠቢቡ ሰሎሞን ‹‹በመከር ወራት የውርጭ ጠል ደስ እንደሚያሰኝ እንዲሁ የታመነ መልእክተኛ ለላኩት ነው፤›› በማለት እንደ መሰለው /ምሳ.፳፭፥፲፫/፣ ይኼ የዕፀዋት ልምላሜ በጎ ምግባር ባላቸው ምእመናንና በመልካም አገልጋዮች ይመሰላል፡

በተጨማሪም ዕፀዋት በዝናም አማካይነት በቅለው መለምለማቸው በስብከተ ወንጌል (ቃለ እግዚአብሔር) ተለውጠው፣ በሃይማኖታቸው ጸንተው፣ በክርስቲያናዊ ምግባር ተግተው፣ በቅዱስ ሥጋው በክቡር ደሙ ተወስነው የሚኖሩ ምእመናንን ሕይወት እና እግዚአብሔር ለሰው ልጆች የሚያድለውን ጸጋና በረከት ያመለክታል፡፡ ‹‹ወይረውዩ እምጠለ ቤትከ፤ ከቤትህ ጠል ይጠጣሉ (ይረካሉ)፤›› እንዲል /መዝ.፴፭፥፰/፡፡ ይኸውም በቤተ መቅደሱ ዘወትር የሚፈተተውን ቅዱስ ሥጋውን፣ ክቡር ደሙን መቀበልና ጠበሉን መጠጣት የሚያስገኘውን መንፈሳዊ ርካታ ይገልጻል፡፡

በዚህ ክፍለ ክረምት የሚለመልሙ ዕፀዋት የመብዛታቸውን ያህል በለስና ወይንን የመሰሉ ተክሎች ክረምት ከገባበት ጊዜ ጀምሮ ደርቀው ይቆዩና በበጋ ወቅት ይለመልማሉ፡፡ እነዚህም በመልካም ዘመን ራሳቸውን ደብቀው የሚኖሩና በመከራ ሰዓት ተነሥተው ወንጌልን የሚሰብኩ የሰማዕታት ምሳሌዎች ናቸው፡፡ በለስና ወይንን የመሰሉ ዕፀዋት በዝናም ጊዜ ደርቀው በፀሐይ ጊዜ እንዲለመልሙ፤ ቅዱሳን ሰማዕታትም በምድራዊ ሹመት፣ በሽልማት ወቅት ተሠውረው፤ ሥቃይና ፈተና በሚበራታበት ጊዜ ምድራዊውን መከራ ተቋቁመው ስለ እውነት (ወንጌል) እየመሰከሩ ራሳቸውን በሰማዕትነት አሳልፈው ይሰጣሉና፡፡ ኹላችንንም እንደ ዕፀዋቱ በወንጌል ዝናም ለምልመን መልካም ፍሬ እንድናፈራ የአምላካችን ቅዱስ ፈቃዱ ይኹንልን፡፡

ይቆየን፡፡

ተስእሎተ ቂሣርያ

ነሐሴ ፰ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ነሐሴ ፯ ቀን ከሚከበሩ በዓላት መካከል ‹‹ተስእሎተ ቂሣርያ›› አንደኛው ነው፡፡ የቃሉ (ሐረጉ) ትርጕም ‹‹በቂሣርያ አገር የቀረበ ጥያቄ›› ማለት ሲኾን ይኸውም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹ሰዎች ማን ይሉኛል?›› ብሎ ደቀ መዛሙርቱን መጠየቁን ያስረዳል፡፡

በቅዱስ ወንጌል እንደ ተጻፈው ጌታችን በቂሣርያ አውራጃ ሐዋርያቱን ሰብስቦ ‹‹ሰዎች የሰውን ልጅ (ኢየሱስ ክርስቶስን) ማን ይሉታል?›› ብሎ ሲጠይቃቸው እነርሱም ‹‹ዮሐንስ፣ ኤልያስ፣ ኤርምያስ ወይም ከነቢያት አንዱ ነው ይላሉ›› የሚል ምላሽ ሰጥተውታል፡፡ እርሱም መልሶ ‹‹እናንተስ ማን ትሉኛላችሁ?›› የሚል ጥያቄ ባቀረበላቸው ጊዜ የሐዋርያት አለቃ ቅዱስ ጴጥሮስ ሐዋርያቱን ወክሎ ‹‹አንተ ውእቱ ክርስቶስ ወልደ እግዚአብሔር ሕያው፤ አንተ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ ነህ›› ብሎ የኢየሱስ ክርስቶስን አምላክነት የሚያስረዳ ምላሽ ሰጥቷል፡፡

የቅዱስ ጴጥሮስ ምላሽም ሰዎች ስለ ክርስቶስ ማንነት ከሚሰጡት ግምትና ከሐዋርያት ዕውቀት በላይ በመኾኑ ጌታችን ‹‹የእኔን አምላክነት ሰማያዊ አባቴ ገለጸልህ እንጂ ሥጋዊ ደማዊ አእምሮ አልገለጸልህም›› በማለት አድንቆለታል፡፡ ከዚህ በኋላ ‹‹አንተ አለት ነህ፤ በአንተ መሠረትነት ቤተ ክርስቲያኔን እሠራታለሁ፡፡ የገሃነም ደጆች (አጋንንት) አይችሏትም፡፡ የመንግሥተ ሰማያትን መክፈቻ እሰጥሃለሁ፡፡ በምድር ያሠርኸው በሰማይም የታሠረ፤ በምድር የፈታኸው በሰማይም የተፈታ ይኾናል›› በማለት ለስብከተ ወንጌል መስፋፋት፣ ለቤተ ክርስቲያናችን መታነፅ፣ ለምእመናን ድኅነት ምክንያት የኾነውን መዓርገ ክህነት ሰጥቶታል /ማቴ.፲፮፥፲፫-፲፱/፡፡

ይህም ሥልጣነ ክህነት በቅዱስ ጴጥሮስ አንጻር ከሐዋርያት ጀምሮ ለሚነሡ አባቶች ካህናት የተሰጠ ሰማያዊ ሀብት ነው፡፡ ዛሬ ምእመናን በኀጢአት ስንሰናከል ከካህናት ፊት ቀርበን የምንናዘዘውና ንስሐ የምንቀበለው፣ እንደዚሁም እየተባረክን ‹‹ይፍቱኝ›› የምንለው ጌታችን ለእነርሱ የሰጣቸውን ሥልጣነ ክህነት መሠረት በማድረግ ነው፡፡ ካህናትም ‹‹ይኅድግ ይፍታሕ ያንጽሕ ወይቀድስ …›› እያሉ ከናዘዙን በኋላ ‹‹እግዚአብሔር ይፍታ›› የሚሉን ከባለቤቱ የማሠር የመፍታት ሥልጣን ስለ ተሰጣቸው ነው፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰዎች ስለ እርሱ የሚናገሩትንም፣ የሚያስቡትንም የሚያውቅ አምላክ ሲኾን በቂሣርያ ሐዋርያቱን ‹‹ሰዎች ማን ይሉኛል›› ብሎ መጠየቁ በአንድ በኩል አላዋቂ ሥጋን መልበሱን ለማጠየቅ፤ በሌላ ምሥጢር ደግሞ ሐዋርያቱን ‹‹እናንተስ ማን ትሉኛላችሁ›› ብሎ በመጠየቅ አምላክ ወልደ አምላክ መኾኑን ለመግለጥና መዓርገ ክህነትን ለሐዋርያትና ለተከታዮቻቸው (ለጳጳሳት፣ ቀሳውስትና ዲያቆናት) ለመስጠት ነው፡፡ ይህም በቅዱስ ጴጥሮስ ምላሽና ጌታችን ለጴጥሮስ በሰጠው ሥልጣን ይታወቃል፡፡

በዚህ በተስእሎተ ቂሣርያ ጌታችን ሐዋርያቱ ማን እንደሚሉት ስለ ማንነቱ ከጠየቃቸው በኋላ ምላሻቸውን ተከትሎ ሥልጣነ ክህነትን መስጠቱ በብሉይ ኪዳን (እግዚአብሔር በሥጋ ከመገለጡ በፊት) አዳም የት እንዳለ እያወቀ ‹‹አዳም ሆይ ወዴት ነህ?›› /ዘፍ.፫፥፲/ ብሎ ከጠየቀውና ያለበትን እንዲናገር ካደረገው በኋላ ‹‹ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ›› የሚል የድኅንት ቃል ኪዳን መግባቱን ያስታውሰናል /ቀሌምንጦስ/፡፡

እንደዚሁም እግዚአብሔር በሦስትነቱ ከአብርሃም ቤት በገባ ጊዜ ሣራ ያለችበትን ቦታ እያወቀ አብርሃምን ‹‹ሚስትህ ሣራ ወዴት ናት?›› ሲል ያለችበትን ቦታ ካናገረው በኋላ ‹‹ሣራ የዛሬ ዓመት ልጅን ታገኛለች›› የሚል በአንድ በኩል የይስሐቅን መወለድ፤ በሌላ በኩል ደግሞ የእግዚአብሔርን ሰው መኾንና የሐዲስ ኪዳንን መመሥረት የሚያበሥር ቃል መናገሩ ከዚህ ትምህርት ጋር ተመሳሳይነት አለው /ዘፍ.፲፰፥፱-፲፭/፡፡

በሐዲስ ኪዳንም አልዓዛር በሞተ ጊዜ የተቀበረበትን ቦታ እያወቀ ‹‹አልዓዛርን ወዴት ቀበራችሁት›› /ዮሐ.፲፩፥፴፯/ ብሎ መካነ መቃብሩን ከጠየቀ በኋላ በሥልጣኑ ከሞት እንዲነሣ ማድረጉም ከተስእሎተ ቂሣርያ ጋርና ከላይ ከጠቀስናቸው ምሳሌዎች ጋር የሚወራረስ ምሥጢር አለው፡፡ ይኼ ኹሉ ቃል እግዚአብሔር ያላወቀ መስሎ እየጠየቀ ሰዎች ስሜታቸውን እንዲገልጡ በማድረግ የልባቸውን መሻትና እምነት መሠረት አድርጎ ሥልጣንን፣ በረከትን፣ ጸጋንና ፈውስን እንደሚያድል የሚያስረዳ ትምህርት ነው፡፡ ለዚህም ጌታችን በመዋዕለ ሥጋዌው በምድር በአካለ ሥጋ ሲመላለስ መዳን እንደሚፈልጉ እያወቀ ‹‹ልትድን ትወዳለህን? (ልትድኚ ትወጃለሽን?) ብሎ እየጠየቀ የልባቸውን መሻት እንዲናገሩ ካደረገ በኋላ እምነታቸውን አይቶ በአምላካዊ ቃሉ ‹‹ፈቀድኩ ንጻሕ /ንጽሒ፤ ፈቅጃለሁ ተፈወስ /ተፈወሺ›› እያለ ለሕሙማነ ሥጋ ወነፍስ ፈውስን ማደሉ ትልቅ ማስረጃ ነው፡፡

የእያንዳንዳችንን የልብ መሻት የሚያውቅ አምላክ እኛንም በቸርነቱ ከደዌ ሥጋ ወነፍስ እንዲፈውሰን ቅዱስ ፈቃዱ ይኹንልን፡፡

ስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ፅንሰተ ማርያም ድንግል

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ነሐሴ ፰ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ ‹‹ቀደሰ ማኅደሮ ልዑል …፤ ልዑል እግዚአብሔር ማደሪያውን መረጠ፤ አከበረ፤ ለየ፤ ቀደሰ …›› /መዝ.፵፭፥፬/ በማለት እንደተናገረው፣ አምላክን በማኅፀኗ ለመሸከም የተመረጠችው ማኅደረ ማለኮት፤ የዓለሙን ቤዛ በመውለዷ ‹‹ቤዛዊተ ዓለም›› እየተባለች የምትጠራው፤ በአምላክ ሕሊና ታስባ ትኖር የነበረችው የድኅነታችን ምክንያት የኾነችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በማኅፀን የተቋጠረችው ነሐሴ ፯ ቀን ነው፡፡ ፅንሰቷም እግዚአብሔር በባረከውና ባከበረው ቅዱስ ጋብቻ በተወሰኑት ወላጆቿ በቅዱስ ኢያቄምና በቅድስት ሐና ሥርዓት ያለው ግንኙነት አማካይነት ነው፡፡ ‹‹ኦ ድንግል አኮ በፍትወተ ደነስ ዘተፀነስኪ አላ በሩካቤ ዘበሕግ እምሐና ወኢያቄም ተወለድኪ፤ ድንግል ሆይ በሥጋዊ ፈቃድ የተፀንሽ አይደለሽም፤ ሕጋዊ በኾነ ሥርዓት ከሐና እና ከኢያቄም ተወለድሽ እንጂ›› እንዲል /ቅዳሴ ማርያም/፡፡

ታሪኩን ለማስታዎስ ያህል የእመቤታችን ቅድመ አያቶቿ ቴክታ እና በጥሪቃ ይህ ቀራቸው የማይባሉ ባለጠጎች እና መካኖች ነበሩ፡፡ በጥሪቃ ሚስቱ ቴክታን ‹‹አንቺ መካን፤ እኔ መካን፡፡ ይህ ኹሉ ገንዘብ ለማን ይኾናል?›› አላት፡፡ ቴክታም ‹‹እግዚአብሔር ከእኔ ልጅ ባይሰጥህ ከሌላ ይሰጥህ ይኾናል፡፡ ሌላ ሚስት አግብተህ ልጅ አትወልድምን?›› ብትለው ‹‹ይህንስ እንዳላደርገው አምላከ እስራኤል ያውቃል›› አላት፡፡ ኹለቱም እያዘኑ ሲኖሩ አንድ ቀን ነጭ እንቦሳ (ጥጃ) ከበረታቸው ስትወጣ፤ እንቦሳይቱ እንቦሳ እየወለደች እስከ ስድስት ልጅ ስትደርስና ስድስተኛዪቱ እንቦሳም ጨረቃን፣ ጨረቃም ፀሐይን ስትወልድ ራእይ አዩ፡፡

ራእያቸውን ለሕልም ተርጓሚ ሲነግሩም ‹‹የጨረቃዪቱ ትርጕም ከፍጡራን በላይ የምትኾን ልጅ እንደምታገኙ የሚያመለክት ነው፡፡ የፀሐይ ነገር ግን አልተገለጠልኝም፡፡ እንደ ነቢይ፣ እንደ ንጉሥ ያለ ይኾናል፤›› አላቸው፡፡ እነርሱም ‹‹ጊዜ ይተርጕመው ብለው›› ወደ ቤታቸው ከተመለሱ በኋላ ቴክታ ሴት ልጅ ወለደች፤ ስሟንም ሄኤሜን አለቻት፡፡ ትርጕሙም ስእለቴን (ምኞቴን) አገኘሁ ማለት ነው፡፡ ሄኤሜን ዴርዴን፤ ዴርዴ ቶናን፤ ቶና ሲካርን፤ ሲካር ሄርሜላን፤ ሄርሜላ ሐናን ወለደች፡፡ ሐና ለዓቅመ ሄዋን ስትደርስም ኢያቄም ለሚባል ደግ ሰው አጋቧት፡፡ እነርሱም እንደ በጥሪቃና ቴክታ መካኖች ነበሩ፡፡ በእስራኤላውያን ባህል መካንነት የእርግማን ምልክት ተደርጎ ይቈጠር ነበርና ሐና እና ኢያቄም ብዙ ዘለፋና ሽሙጥ ይደርስባቸው ነበር፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን መሥዋዕት ለማቅረብ ወደ ቤተ መቅደስ ቢሔዱ የዘመኑ ሊቀ ካህናት ሮቤል መካን መኾናቸውን ያውቅ ነበርና ‹‹እናንተማ ‹ብዙ ተባዙ› ብሎ እግዚአብሔር ለአዳም የነገረውን ያስቀረባችሁ ርጉማን አይደላችሁምን? እግዚአብሔር ቢጠላችሁ እንጂ ቢወዳችሁማ ልጅ ይሰጣችሁ አልነበረምን?›› ብሎ መሥዋዕታቸውን ሳይቀበላቸው በመቅረቱ፤ አንድም ከአዕሩገ እስራኤል (ከአረጋውያን እስራኤላውያን) የተወለዱ ሰዎች የሚመገቡትን ተረፈ መሥዋዕት እንዳይመገቡ በመከልከሉ እያዘኑ ሲመለሱ ከልጆቻቸው ጋር የሚጫወቱ ርግቦችንና አብበው ያፈሩ ዕፀዋትን ሐና ተመለከተች፡፡ እርሷም ‹‹ርግቦችን በባሕርያቸው መራባት እንዲችሉ፤ ዕፀዋትን አብበው እንዲያፈሩ የምታደርግ ጌታ እኔን ለምን ልጅ ነሳኸኝ?›› ብላ አዘነች፡፡

ከቤታቸው ሲደርሱም ‹‹እግዚአብሔር ልጅ ቢሰጠን ወንድ ከኾነ ለቤተ እግዚአብሔር ምንጣፍ አንጣፊ፣ መጋረጃ ጋራጅ ኾኖ ሲያገለግል ይኑር፤ ሴት ብትኾንም መሶበ ወርቅ ሰፍታ፣ መጋረጃ ፈትላ ስታገለግል ትኑር›› ብለው ከተሳሉ በኋላ ሐምሌ ፴ ቀን ሐና ለኢያቄም ‹‹በሕልሜ ፀምር (መጋረጃ) ሲያስታጥቁህ፤ በትርህ አፍርታ ፍጥረት ኹሉ ሲመገባት አየሁ›› ብላ ያየቸውን ራእይ ነገረችው፡፡ ኢያቄም ደግሞ ለሐና ‹‹ጸዓዳ ረግብ ሰባቱን ሰማያት ሰንጥቃ መጥታ በራስሽ ላይ ስታርፍ፣ በቀኝ ጆሮሽ ገብታ በማኅፀንሽ ስታድር አየሁ›› ብሎ ያየውን ራእይ ነገራት፡፡ ሕልም ተርጓሚው ‹‹ደግ ልጅ ትወልዳላችሁ›› ባላቸው ጊዜም ‹‹አንተ አልፈታኸውም፤ ጊዜ ይፍታው›› ብለው ተመልሰዋል፡፡

ከዚህ በኋላ የእግዚአብሔር መልአክ ‹‹ደግ ልጅ ትወልዳላችሁ›› ብሎ ነግሯቸው ሐዲስ ኪዳን ሊበሠር፤ ጌታችን ሊፀነስ ፲፬ ያህል ዓመታት ሲቀሩ ነሐሴ ፯ ቀን በፈቃደ እግዚአብሔር እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተፀንሳለች፡፡ እመቤታችን በሐና ማኅፀን ውስጥ ሳለች ከተደረጉ ተአምራት መካከልም በርሴባ የምትባል አንድ ዓይና ሴት (አክስቷ) ሐናን ‹‹እግዚአብሔር በረድኤት ጐበኘሽ መሰለኝ ጡቶችሽ ጠቁረዋል፤ ከንፈሮችሽ አረዋል›› ብላ ማኅፀኗን በዳሰሰችበት እጇ ብታሸው ዓይኗ በርቶላታል፡፡ ይህንን አብነት አድርገውም ብዙ ሕሙማን ከደዌያቸው ተፈውሰዋል፡፡

ዳግመኛም ሳምናስ የሚባል ያጎቷ ልጅ በሞተ ጊዜ ሐና የአልጋውን ሸንኮር ይዛ ስታለቅስ ጥላዋ ቢያርፍበት ከሞት ተነሥቶ ‹‹ሰላም ለኪ ኦ እምሔውቱ ለዘገብረ ሰማየ ወምድረ፤ ሰማይና ምድርን የፈጠረው አምላክ አያቱ ሐና ሆይ ሰላም ላንቺ ይኹን›› ብሎ ሕልም ተርጓሚው ያልፈታውን ራእይ በመተርጐም ከሐና እመቤታችን፤ ከእመቤታችን ደግሞ እውነተኛ ፀሐይ የተባለው ክርስቶስ እንሚወለድ አስቀድሞ ተናግሯል፡፡ /ምንጭ፡- ቅዳሴ ማርያም አንድምታ ትርጓሜ፣ ፭፥፴፰/፡፡

በአጠቃላይ አባ ሕርያቆስ በቅዳሴው ‹‹ኦ ማርያም በእንተዝ ናፈቅረኪ ወናዓብየኪ እስመ ወለድኪ ለነ መብልዐ ጽድቅ ዘበአማን ወስቴ ሕይወት ዘበአማን፤ ማርያም ሆይ እውነተኛውን ምግብ፣ እውነተኛውን መጠጥ አስገኝተሽልናልና እናከብርሻለን፤ እናገንሻለን፤›› በማለት እንደ አመሰገናት እኛም ዘለዓለማዊ ሕይወት የሚሰጠውን፤ ከሞተ ሥጋ ከሞተ ነፍስ ማዳን የሚቻለውን፤ እውነተኛውን ምግበ ሥጋ ወነፍስ ኢየሱስ ክርስቶስን ስለወለደችልን ‹‹እናታችን፣ አማላጃችን፣ የድኅነታችን ምክንያት፣ ወዘተ›› እያልን እመቤታችንን እናከብራታለን፤ እናገናታለን፤ እናመሰግናታለን፡፡ እናቱን በአማላጅነት፤ ራሱን በቤዛነት ለሰጠን ለልዑል እግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይድረሰው፤ የእመቤታችን በረከት አይለየን፡፡

ፅንሰተ ድንግል ወተስእሎተ ቂሣርያ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ነሐሴ ፮ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በነሐሴ ወር በሰባተኛው ቀን ከሚከብሩ በዓላት መካከል በዛሬው ዝግጅታችን የእመቤታችንን ፅንሰት እና ተስእሎተ ቂሣርያን የተመለከተ ጽሑፍ ይዘንላችሁ ቀርበናል፡፡ በመጀመሪያም ፅንሰተ ድንግል ማርያምን እናስቀድም፤

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እኛን ለማዳን ሲል በዕለተ ዓርብ በመስቀል ላይ የቈረሰውና ያፈሰሰው፤ እርሱን የበሉና የጠጡ ኹሉ መንግሥቱን የሚወርሱበት፤ ዘወትር በቤተ መቅደሱ የሚፈተተው ቅዱስ ሥጋውና የሚቀዳው ክቡር ደሙ ከንጽሕተ ንጹሐን፣ ከቅድስተ ቅዱሳን ከወላዲተ አምላክ ድንግል ማርያም የተዋሐደው ሥጋና ደም ነው፡፡ እመቤታችንን እናታችን፣ አማላጃችን፣ የድኅነታችን ምክንያት፣ ወዘተ እያልን የምናከብራት፣ የምናገናት፣ የምንወዳት ዘለዓለማዊ ሕይወት የሚሰጠውን፤ ከሞተ ሥጋ ከሞተ ነፍስ ማዳን የሚቻለውን፤ እውነተኛውን ምግበ ሥጋ ወነፍስ ኢየሱስ ክርስቶስን ስለወለደችልን ነው፡፡ ‹‹ኦ ማርያም በእንተዝ ናፈቅረኪ ወናዓብየኪ እስመ ወለድኪ ለነ መብልዐ ጽድቅ ዘበአማን ወስቴ ሕይወት ዘበአማን፤ ማርያም ሆይ እውነተኛውን ምግብ፣ እውነተኛውን መጠጥ አስገኝተሽልናልና እናከብርሻለን፤ እናገንሻለን፤›› እንዳለ አባ ሕርያቆስ በቅዳሴ ማርያም፡፡

ቅዱስ ዳዊት ‹‹ቀደሰ ማኅደሮ ልዑል …፤ ልዑል እግዚአብሔር ማደሪያውን መረጠ፤ አከበረ፤ ለየ፤ ቀደሰ …›› /መዝ.፵፭፥፬/ በማለት እንደተናገረው አምላክን በማኅፀኗ ለመሸከም የተመረጠችው ማኅደረ ማለኮት ቅድስት ድንግል ማርያም የተፀነሰችው ነሐሴ ፯ ቀን ነው፡፡ ፅንሰቷም እግዚአብሔር በባረከውና ባከበረው ቅዱስ ጋብቻ በተወሰኑት ወላጆቿ በቅዱስ ኢያቄምና በቅድስት ሐና ሥርዓት ያለው ግንኙነት አማካይነት ነው፡፡ ‹‹ኦ ድንግል አኮ በፍትወተ ደነስ ዘተፀነስኪ አላ በሩካቤ ዘበሕግ እምሐና ወኢያቄም ተወለድኪ፤ ድንግል ሆይ በሥጋዊ ፈቃድ የተፀንሽ አይደለሽም፤ ሕጋዊ በኾነ ሥርዓት ከሐና እና ከኢያቄም ተወለድሽ እንጂ›› እንዲል /ቅዳሴ ማርያም/፡፡

ታሪኩን ለማስታዎስ ያህልም የእመቤታችን ቅድመ አያቶቿ ቴክታ እና በጥሪቃ ይህ ቀራቸው የማይባሉ ባለጠጎች እና መካኖች ነበሩ፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን በጥሪቃ ከቤተ መዛግብት ገብቶ የገንዘባቸውንና የንብረታቸውን ብዛት አይቶ ሚስቱ ቴክታን ‹‹አንቺ መካን፤ እኔ መካን፡፡ ይህ ኹሉ ገንዘብ ለማን ይኾናል?›› አላት፡፡ ቴክታም ‹‹እግዚአብሔር ከእኔ ልጅ ባይሰጥህ ከሌላ ይሰጥህ ይኾናል፡፡ ሌላ ሚስት አግብተህ ልጅ አትወልድምን?›› ባለችው ጊዜ ‹‹ይህንስ እንዳላደርገው አምላከ እስራኤል ያውቃል›› አላት፡፡ በዚህ ጊዜ ኹለቱም እያዘኑ ሳሉ ነጭ እንቦሳ (ጥጃ) ከበረታቸው ስትወጣ፤ እንቦሳይቱ እንቦሳ እየወለደች እስከ ስድስት ልጅ ስትደርስና ስድስተኛዪቱ እንቦሳም ጨረቃን፣ ጨረቃም ፀሐይን ስትወልድ ራእይ አዩ፡፡

ራእያቸውን ለሕልም ተርጓሚ ሲነግሩም ‹‹የጨረቃዪቱ ትርጕም ከፍጡራን በላይ የምትኾን ልጅ እንደምታገኙ የሚያመለክት ነው፡፡ የፀሐይ ነገር ግን አልተገለጠልኝም፡፡ እንደ ነቢይ፣ እንደ ንጉሥ ያለ ይኾናል፤›› አላቸው፡፡ እነርሱም ‹‹ጊዜ ይተርጕመው ብለው›› ወደ ቤታቸው ከተመለሱ በኋላ ቴክታ ፀንሳ ሴት ልጅ ወለደች፤ ስሟንም ሄኤሜን አለቻት፡፡ ትርጕሙም ስእለቴን (ምኞቴን) አገኘሁ ማለት ነው፡፡ ሄኤሜን ዴርዴን፤ ዴርዴ ቶናን፤ ቶና ሲካርን፤ ሲካር ሄርሜላን፤ ሄርሜላ ሐናን ወለደች፡፡ ሐና ለዓቅመ ሄዋን ስትደርስም ኢያቄም ለሚባል ደግ ሰው አጋቧት፡፡ እነርሱም እንደ በጥሪቃና ቴክታ መካኖች ነበሩ፡፡ በእስራኤላውያን ባህል መካንነት የእርግማን ምልክት ተደርጎ ይቈጠር ነበርና ሐና እና ኢያቄም ብዙ ዘለፋና ሽሙጥ ይደርስባቸው ነበር፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን መሥዋዕት ለማቅረብ ወደ ቤተ መቅደስ ቢሔዱ የዘመኑ ሊቀ ካህናት ሮቤል መካን መኾናቸውን ያውቅ ነበርና ‹‹እናንተማ ‹ብዙ ተባዙ› ብሎ እግዚአብሔር ለአዳም የነገረውን ያስቀረባችሁ ርጉማን አይደላችሁምን? እግዚአብሔር ቢጠላችሁ እንጂ ቢወዳችሁማ ልጅ ይሰጣችሁ አልነበረምን?›› ብሎ መሥዋዕታቸውን ሳይቀበላቸው በመቅረቱ፤ አንድም ከአዕሩገ እስራኤል (ከአረጋውያን እስራኤላውያን) የተወለዱ ሰዎች የሚመገቡትን ተረፈ መሥዋዕት እንዳይመገቡ በመከልከሉ እያዘኑ ሲመለሱ ከልጆቻቸው ጋር የሚጫወቱ ርግቦችንና አብበው ያፈሩ ዕፀዋትን ሐና በተመለከተች ጊዜ ‹‹ርግቦችን በባሕርያቸው መራባት እንዲችሉ፤ ዕፀዋትን አብበው እንዲያፈሩ የምታደርግ ጌታ እኔን ለምን ልጅ ነሳኸኝ?›› ብላ አዘነች፡፡

ከቤታቸው ሲደርሱም ‹‹እግዚአብሔር ልጅ ቢሰጠን ወንድ ከኾነ ለቤተ እግዚአብሔር ምንጣፍ አንጣፊ፣ መጋረጃ ጋራጅ ኾኖ ሲያገለግል ይኑር፤ ሴት ብትኾንም መሶበ ወርቅ ሰፍታ፣ መጋረጃ ፈትላ ስታገለግል ትኑር›› ብለው ከተሳሉ በኋላ ሐምሌ ፴ ቀን ሐና ለኢያቄም ‹‹በሕልሜ ፀምር (መጋረጃ) ሲያስታጥቁህ፤ በትርህ አፍርታ ፍጥረት ኹሉ ሲመገባት አየሁ›› ብላ ያየቸውን ራእይ ነገረችው፡፡ ኢያቄም ደግሞ ለሐና ‹‹ጸዓዳ ረግብ ሰባቱን ሰማያት ሰንጥቃ መጥታ በራስሽ ላይ ስታርፍ፣ በቀኝ ጆሮሽ ገብታ በማኅፀንሽ ስታድር አየሁ›› ብሎ ያየውን ራእይ ነገራት፡፡ ሕልም ተርጓሚው ‹‹ደግ ልጅ ትወልዳላችሁ›› ባላቸው ጊዜም ‹‹አንተ አልፈታኸውም፤ ጊዜ ይፍታው›› ብለው ተመልሰዋል፡፡

ከዚህ በኋላ የእግዚአብሔር መልአክ መጥቶ ‹‹ደግ ልጅ ትወልዳላችሁ›› ብሎ ነግሯቸው ሐዲስ ኪዳን ሊበሠር፤ ጌታችን ሊፀነስ ፲፬ ያህል ዓመታት ሲቀሩ ነሐሴ ፯ ቀን በፈቃደ እግዚአብሔር እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተፀንሳለች፡፡ እመቤታችን በሐና ማኅፀን ውስጥ ሳለች ከተደረጉ ተአምራት መካከልም በርሴባ የምትባል አንድ ዓይና ሴት (አክስቷ) ሐናን ‹‹እግዚአብሔር በረድኤት ጐበኘሽ መሰለኝ ጡቶችሽ ጠቁረዋል፤ ከንፈሮችሽ አረዋል›› ብላ ማኅፀኗን በዳሰሰችበት እጇ ብታሸው ዓይኗ በርቶላታል፡፡ ይህንን አብነት አድርገውም ብዙ ሕሙማን ከደዌያቸው ተፈውሰዋል፡፡ ዳግመኛም ሳምናስ የሚባል ያጎቷ ልጅ በሞተ ጊዜ ሐና የአልጋውን ሸንኮር ይዛ ስታለቅስ ጥላዋ ቢያርፍበት ከሞት ተነሥቶ ‹‹ሰላም ለኪ ኦ እምሔውቱ ለዘገብረ ሰማየ ወምድረ፤ ሰማይና ምድርን የፈጠረው አምላክ አያቱ ሐና ሆይ ሰላም ላንቺ ይኹን›› ብሎ ሕልም ተርጓሚው ያልፈታውን ራእይ በመተርጐም ከሐና እመቤታችን፤ ከእመቤታችን ደግሞ እውነተኛ ፀሐይ የተባለው ክርስቶስ እንሚወለድ አስቀድሞ ተናግሯል፡፡ /ምንጭ፡- ቅዳሴ ማርያም አንድምታ ትርጓሜ፣ ፭፥፴፰/፡፡

በየዓመቱ ነሐሴ ፯ ቀን የሚዘከረው ሌላኛው በዓል ደግሞ ‹‹ተስእሎተ ቂሣርያ›› የሚባለው የጌታችን በዓል ነው፤ የቃሉ (ሐረጉ) ትርጕም በቂሣርያ አገር የቀረበ ጥያቄ ማለት ሲኾን ይኸውም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹ሰዎች ማን ይሉኛል?›› ብሎ ደቀ መዛሙርቱን መጠየቁን ያስረዳል፡፡ በቅዱስ ወንጌል እንደ ተጻፈ ጌታችን በቂሣርያ አውራጃ ሐዋርያቱን ሰብስቦ ‹‹ሰዎች የሰውን ልጅ (ኢየሱስ ክርስቶስን) ማን ይሉታል?›› ብሎ ሲጠይቃቸው እነርሱም ‹‹ዮሐንስ፣ ኤልያስ፣ ኤርምያስ ወይም ከነቢያት አንዱ ነው ይላሉ›› የሚል ምላሽ ሰጥተውታል፡፡ እርሱም መልሶ ‹‹እናንተስ ማን ትሉኛላችሁ?›› የሚል ጥያቄ ባቀረበላቸው ጊዜ የሐዋርያት አለቃ ቅዱስ ጴጥሮስ ሐዋርያቱን ወክሎ ‹‹አንተ ውእቱ ክርስቶስ ወልደ እግዚአብሔር ሕያው፤ አንተ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ ነህ›› ብሎ የኢየሱስ ክርስቶስን አምላክነት የሚያስረዳ ምላሽ ሰጥቷል፡፡

የቅዱስ ጴጥሮስ ምላሽም ሰዎች ስለ ክርስቶስ ማንነት ከሚሰጡት ግምትና ከሐዋርያት ዕውቀት በላይ በመኾኑ ጌታችን ‹‹የእኔን አምላክነት ሰማያዊ አባቴ ገለጸልህ እንጂ ሥጋዊ ደማዊ አእምሮ አልገለጸልህም›› በማለት አድንቆለታል፡፡ ከዚህ በኋላ ‹‹አንተ አለት ነህ፤ በአንተ መሠረትነት ቤተ ክርስቲያኔን እሠራታለሁ፡፡ የገሃነም ደጆች (አጋንንት) አይችሏትም፡፡ የመንግሥተ ሰማያትን መክፈቻ እሰጥሃለሁ፡፡ በምድር ያሠርኸው በሰማይም የታሠረ፤ በምድር የፈታኸው በሰማይም የተፈታ ይኾናል›› በማለት ለስብከተ ወንጌል መስፋፋት፣ ለቤተ ክርስቲያናችን መታነፅ፣ ለምእመናን ድኅነት ምክንያት የኾነውን መዓርገ ክህነት ሰጥቶታል /ማቴ.፲፮፥፲፫-፲፱/፡፡

ይህም ሥልጣነ ክህነት በቅዱስ ጴጥሮስ አንጻር ከሐዋርያት ጀምሮ ለሚነሡ አባቶች ካህናት የተሰጠ ሰማያዊ ሀብት ነው፡፡ ዛሬ ምእመናን በኀጢአት ስንሰናከል ከካህናት ፊት ቀርበን የምንናዘዘውና ንስሐ የምንቀበለው፣ እንደዚሁም እየተባረክን ‹‹ይፍቱኝ›› የምንለው ጌታችን ለእነርሱ የሰጣቸውን ሥልጣነ ክህነት መሠረት በማድረግ ነው፡፡ ካህናትም ‹‹ይኅድግ ይፍታሕ ያንጽሕ ወይቀድስ …›› እያሉ ከናዘዙን በኋላ ‹‹እግዚአብሔር ይፍታ›› የሚሉን ከባለቤቱ የማሠር የመፍታት ሥልጣን ስለ ተሰጣቸው ነው፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰዎች ስለ እርሱ የሚናገሩትንም፣ የሚያስቡትንም የሚያውቅ አምላክ ሲኾን በቂሣርያ ሐዋርያቱን ‹‹ሰዎች ማን ይሉኛል›› ብሎ መጠየቁ በአንድ በኩል አላዋቂ ሥጋን መልበሱን ለማጠየቅ፤ በሌላ ምሥጢር ደግሞ ሐዋርያቱን ‹‹እናንተስ ማን ትሉኛላችሁ›› ብሎ በመጠየቅ አምላክ ወልደ አምላክ መኾኑን ለመግለጥና መዓርገ ክህነትን ለሐዋርያትና ለተከታዮቻቸው (ለጳጳሳት፣ ቀሳውስትና ዲያቆናት) ለመስጠት ነው፡፡ ይህም በቅዱስ ጴጥሮስ ምላሽና ጌታችን ለጴጥሮስ በሰጠው ሥልጣን ይታወቃል፡፡

በዚህ በተስእሎተ ቂሣርያ ጌታችን ሐዋርያቱ ማን እንደሚሉት ስለ ማንነቱ ከጠየቃቸው በኋላ ምላሻቸውን ተከትሎ ሥልጣነ ክህነትን መስጠቱም በብሉይ ኪዳን (እግዚአብሔር በሥጋ ከመገለጡ በፊት) አዳም የት እንዳለ እያወቀ ‹‹አዳም ሆይ ወዴት ነህ?›› /ዘፍ.፫፥፲/ ብሎ ከጠየቀውና ያለበትን እንዲናገር ካደረገው በኋላ ‹‹ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ›› የሚል የድኅንት ቃል ኪዳን መግባቱን ያስታውሰናል /ቀሌምንጦስ/፡፡ እንደዚሁም እግዚአብሔር በሦስትነቱ ከአብርሃም ቤት በገባ ጊዜ ሣራ ያለችበትን ቦታ እያወቀ አብርሃምን ‹‹ሚስትህ ሣራ ወዴት ናት?›› ሲል ያለችበትን ቦታ ካናገረው በኋላ ‹‹ሣራ የዛሬ ዓመት ልጅን ታገኛለች›› የሚል በአንድ በኩል የይስሐቅን መወለድ፤ በሌላ በኩል ደግሞ የእግዚአብሔርን ሰው መኾንና የሐዲስ ኪዳንን መመሥረት የሚያበሥር ቃል መናገሩ ከዚህ ትምህርት ጋር ተመሳሳይነት አለው /ዘፍ.፲፰፥፱-፲፭/፡፡

በሐዲስ ኪዳንም አልዓዛር በሞተ ጊዜ የተቀበረበትን ቦታ እያወቀ ‹‹አልዓዛርን ወዴት ቀበራችሁት›› /ዮሐ.፲፩፥፴፯/ ብሎ መካነ መቃብሩን ከጠየቀ በኋላ በሥልጣኑ ከሞት እንዲነሣ ማድረጉም ከተስእሎተ ቂሣርያ ጋርና ከላይ ከጠቀስናቸው ምሳሌዎች ጋር የሚወራረስ ምሥጢር አለው፡፡ ይኼ ኹሉ ቃል እግዚአብሔር ያላወቀ መስሎ በመጠየቅ የሰዎችን ስሜት እንደሚገልጥና የልባቸውን መሻትና እምነት መሠረት አድርጎ ሥልጣንን፣ በረከትንና ጸጋን እንደሚያድል የሚያስረዳ ትምህርት ነው፡፡ ለዚህም ጌታችን በመዋዕለ ሥጋዌው በምድር በአካለ ሥጋ ሲመላለስ መዳን እንደሚፈልጉ እያወቀ ‹‹ልትድን ትወዳለህን? (ልትድኚ ትወጃለሽን?) እያለ በመጠየቅ የልባቸውን መሻት እንዲናገሩ ካደረገ በኋላ እምነታቸውን አይቶ ‹‹ፈቀድኩ ንጻሕ /ንጽሒ፤ ፈቅጃለሁ ተፈወስ /ተፈወሺ›› እያለ በአምላካዊ ቃሉ ለሕሙማነ ሥጋ ወነፍስ ፈውስን ማደሉ ትልቅ ማስረጃ ነው፡፡

በአጠቃላይ ‹‹እመቤታችን ከእርሷ እንድትወለድ ዐውቆ አዳም ሔዋንን ሕይወቴ ነሽ ይላት ነበር›› እንደ ተባለው የኹላችንም ሕይወት፤ የዓለሙን ቤዛ በመውለዷ ቤዛዊተ ዓለም እየተባለች የምትጠራው፤ በአምላክ ሕሊና ታስባ ትኖር የነበረችው የድኅነታችን ምክንያት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በማኅፀን የተቋጠረችው፤ ዳግመኛም በቂሣርያ ሐዋርያት ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ አምላክነት የመሰከሩት፣ እርሱም ሥልጣነ ክህነትን የሰጣቸው በዚህች ዕለት ነውና በመላው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት በየዓመቱ ነሐሴ ፯ ቀን በድምቀት ይከበራል፡፡ እናቱን በአማላጅነት፤ ራሱን በቤዛነት ለሰጠን ለልዑል እግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይድረሰው፤ የእመቤታችን በረከት አይለየን፡፡

በፕሪንስተን ዩኒቨርሲቲ፣ በኖቲንግሃምና በጎንደር ከተሞች ዐውደ ጥናቶች ተካሔዱ

ነሐሴ ፬ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በአሜሪካ፣ በአውሮፓና በጎንደር ማእከላት

IMG_4429

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የአሜሪካ ማእከል በፕሪንስተን ዩኒቨርሲቲ ልዩ ዐውደ ጥናት እንደሚያካሒድ ሐምሌ ፮ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ባወጣነው ዘገባ ማስነበባችን ይታወሳል፡፡

በዚህ መሠረት ማእከሉ ከፕሪንስተን ዩኒቨርሲቲ እና የሴሜቲክና የአፍሮ እስያ ከፍተኛ ምርምርና ጥናት ተቋም (The Institute for Advanced Semitic Studies and Afro Asiatic Studies) ክፍል ጋር በመተባበር ባዘጋጀው መርሐ ግብር ‹‹የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አስተዋጽዖ›› በሚል ርእስ ሐምሌ ፳፬ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በፕሪንስተን ዩኒቨርሲቲ ልዩ ዐውደ ጥናት ተካሒዷል።

በዐውደ ጥናቱ በጥናት አቅራቢነት የተሳተፉትን ፕሮፌሰር ኤፍሬም ይስሐቅን ጨምሮ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መምህራንና ካህናት፣ የማኅበረ ቅዱሳን አባላት፣ የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች፣ የፕሪንስተን ዩኒቨርሲቲ ምሁራንና ጥሪ የተደረገላቸው የውጭ አገር ዜጎች ተገኝተዋል፡፡

በአማርኛ እና በእንግሊዝኛ ቋንቋዎች በተካሔደው በዚህ ዐውደ ጥናት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰላምና ልማትን በማጠናከር፤ የተለያዩ የእምነት ተቋማትና የኅብረተሰብ ክፍሎች ተቻችለውና ተከባብረው ለዘመናት እንዲኖሩ በማስቻል፤ እንደዚሁም በሥነ ጽሑፍ፣ በቋንቋ፣ በዜማ ጥበብ እና ልዩ ልዩ ዘርፎች ለዓለም ያበረከተችውን አስተዋጽዖ የሚዳስሱ ዝግጅቶች ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል።

full image
አንዳንድ የዐውደ ጥናቱ ተሳታፊዎች በሰጡት አስተያየት ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ለዓለም የማስተዋወቁን ሥራ ማኅበሩ አጠናክሮ እንዲቀጥል አሳስበው እንደዚህ ዓይነቱ የዓውደ ጥናት መርሐ ግብር ለቤተ ክርስቲያን ብቻ ሳይኾን በመላው ዓለም ለሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ኹሉ ትልቅ ርካታን እንደሚሰጥና የአገራችንን ታሪክ ለዓለም ለማስተዋወቅም ከፍተኛ ጥቅም እንደሚኖረው ጠቁመዋል።

በመጨረሻም ለዐውደ ጥናቱ መሳካት ቦታ በማመቻቸት፣ ቁሳቁስ በማሟላትና አስተርጓሚ ባለሙያዎችን በመመደብ የፕሪንስተን ዩኒቨርሲቲ ላደረገው ከፍተኛ ትብብር እንዲሁም ለጥናት አቅራቢዎችና ተሳታፊዎች የማኅበሩ ተወካይ ምስጋናቸውን አቅርበው ወደፊትም ይህን መሰል ዓውደ ጥናቶችን ማእከሉ በዓለም አቀፍ ደረጃ ዕውቅና ካላቸው ዩኒቨርሲቲዎችና ተቋማት ጋር በተጠናከረ ኹኔታ እንደሚያካሒድ አስታውቀዋል፡፡

በተያያዘ ዜና የእንግሊዝ ንዑስ ማእከል ‹‹መዝሙሮቻችን ከየት ወዴት›› በሚል ርእስ ሐምሌ ፳፬ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም የኖቲንግሃምና የአቅራቢያ ከተሞች ካህናትና ምእመናን፣ የሰንበት ት/ቤት መዘምራንና የንዑስ ማእከሉ አባላት በተገኙበት በኖቲንግሃም ከተማ የግንዛቤ ማስጨበጫ መርሐ ግብር ማካሔዱን የአውሮፓ ማእከል አስታውቋል።

M

የመርሐ ግብሩ ዋና ዓላማም በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስም እየታተሙ ገበያ ላይ የሚዉሉ የአማርኛ መዝሙራት ከያሬዳዊ ዜማ ጋር ያላቸውን ግንኙነት ማጥናትና የመፍትሔ አቅጣጫዎችን ማመላከት ሲኾን በዕለቱ በሦስት ዋና ዋና አርእስት ላይ ያተኮሩ ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበዋል፡፡ በእያንዳንዱ ገለጻ ላይም በአራቱ ወንጌላውያን ስም የተሰየሙ የቡድን ውይይቶች ተካሒደዋል።

በመርሐ ግብሩ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ዜማ፤ በአማርኛ መዝሙራት የይዘት ችግሮችና በቅዱስ ያሬድ ታሪክና ዜማዎቹ ላይ ያተኮረ ጥናታዊ ዘገባ በሊቀ ዲያቆናት ልዩ ወዳጅ፤ ‹‹የአማርኛ መዝሙራት በተለያዩ አዝማናት›› በሚል ርእስ በመጋቤ ሠናይ ሳምሶን ሰይፈ፤ ‹‹በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስም የወጡ መዝሙራት፣ የመናፍቃን መዝሙራት ተመሳሳይነትና ምን እናድርግ›› በሚል ርእስ በዲ/ን ዶ/ር አዳነ ካሣ ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበዋል።

Publication1

የመጀመሪያዉ ዙር የግንዛቤ ማስጨበጫ መርሐ ግብር በጥር ወር ፳፻፰ ዓ.ም በበዓለ ጥምቀት ዋዜማ በበርሚንግሃም ከተማ ተዘጋጅቶ የነበረ ሲኾን በኖቲንግሃም ከተማ የተዘጋጀው ይህ መርሐ ግብር ሁለተኛው ዙር መኾኑን ከእንግሊዝ ንዑስ ማእከል የተላከልን መረጃ ያመለክታል።

በጉባኤው ላይ የተገኙ ምእመናን በማጠቃለያዉ ላይ በሰጡት አስተያየት መሠረትም በ፳፻፱ ዓ.ም ሦስተኛ ዙር መርሐ ግብር በለንደን ከተማ ለማካሔድ ዕቅድ መያዙንም ንዑስ ማእከሉ ጨምሮ ገልጾልናል።

በመጨረሻም የአዉሮፓ ማእከል ትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ክፍል፤ የእንግሊዝ ንዑስ ማእከል አባላት፤ የልዩ ልዩ አብያተ ክርስቲያናት አገልጋይ ካህናትና ምእመናን ለመርሐ ግብሩ መሳካት ላበረከቱት ልዩ ልዩ አስተዋጽዖ ንዑስ ማእከሉ በእግዚአብሔር ስም ከፍ ያለ ምስጋና አቅርቧል።

በተመሳሳይ የአገር ውስጥ ዜና የጎንደር ማእከል ሙያ አገልግሎት ክፍል ከሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት እና ከጎንደር ከተማ አስተዳደር ባህል እና ቱሪዝም መምሪያ ጋር በመተባበር በጎንደር ከተማ ሲኒማ አዳራሽ ሐምሌ ፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም የዐውደ ጥናት መርሐ ግብር ማካሔዱን የጎንደር ማእከል ዘግቧል፡፡

ማእከሉ ለዝግጅት ክፍላችን እንዳስታወቀው በዐውደ ጥናቱ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ የዩኒቨርሲቲ መምህራን እና የማኅበሩ አባላት የተገኙ ሲኾን የዐውደ ጥናቱ ዓላማም መልካም እና መልካም ያልኾኑ ጉዳዮችን በመመርመር ለቤተ ክርስቲያን ውስጣዊ እና ውጫዊ ችግሮች መፍትሔዎችን ለመጠቆም መኾኑን የጎንደር ማእከል የሙያ አገልግሎት ክፍል ሰብሳቢ ዶ/ር አገኘሁ ተስፋ ተናግረዋል፡፡

ጥናት እና ምርምር ለቤተ ክርስቲያን ያለውን ፋይዳ የተመለከተ ጥናታዊ ጽሑፍ ያቀረቡት ዶ/ር መሠረት ካሤ ጥናትና ምርምር የጎደለውን ለመሙላት፣ የተበተነውን ለመሰብሰብ፣ የተጎዳውን ለመጠገን፣ የጠፋውን ለመፈለግ፣ የተቀበረውን ለማውጣት ዓይነተኛ መንገድ መኾኑን ገልጸው ‹‹የአገራችን የኪነ ጥበብ፣ የሕግ፣ የዘመን አቈጣጠር፣ የባህል እና የማኅበራዊ ሕይወት ዕውቀቶች እና ተግባራዊ ልምምዶች በቀደሙት የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት የተቀመሩ የምርምር ውጤቶች ናቸው›› ሲሉ አስረድተዋል፡፡

ሌላኛዋ ጥናት አቅራቢ ወ/ሪት መሠረት ሐሰን ደግሞ ‹‹ሉላዊነት በባህል እና በእምነት ላይ ያለው ተጽዕኖ›› በሚለው ጥናታቸው በአገራችን በኢትዮጵያ እየተለመዱ የመጡት ከትዳር አጋር ውጭ ጾታዊ ግንኙነት መፈጸም፣ ግብረ ሰዶም፣ ሥርዓት ያጣ አለባበስ፣ ወዘተ የመሳሰሉት ተግባራት የሴኪዩላር ሂዩማኒዝም ምልክቶች መኾናውን አስገንዝበዋል፡፡

አቶ ማርሸት ግርማይ በበኩላቸው ‹‹Rethinking Ethiopian Educational System from the Ethiopian Orthodox Church፤ የኢትጵያን ሥርዓተ ትምህርት ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓተ ትምህርት አንጻር እንደገና ማየት›› በሚል ርእስ ባቀረቡት ጥናታቸው ዘመናዊው ትምህርት ከቤተ ክርስቲያን ሥርዓተ ትምህርት ተሞክሮ መውሰድ እንደሚገባው ጠቁመዋል፡፡

የጎንደር ማእከልም ለጥናቱ መሳካት ልዩ ልዩ አስተዋጽዖ ያበረከቱትንና ጥናት አቅራቢዎችን በእግዚአብሔር ስም አመስግኗል፡፡

ከየማእከላቱ የደረሱን ዘገባዎች እንዳስታወሱት ኹሉም ዐውደ ጥናቶች በአባቶች ጸሎት ተጀምረው በአባቶች ጸሎት ተፈጽመዋል፡፡

ስለ ሀገራችን ወቅታዊ ሁኔታ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የተሰጠ መግለጫ

ነሐሴ ፫ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

.jpj

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን

‹‹ወሰላሙ ለክርስቶስ ይጽናዕ በልብክሙ ዘሎቱ ተጸዋዕክሙ በአሐዱ ሥጋ፤ በአንድ አካል የተጠራችሁለት የክርስቶስ ሰላም በልባችሁ ይጽና፤›› (ቆላ 3÷15)::

ይህ ቃል ሰው ሁሉ ለሰላም እንደተጠራ፣ ልቡንም ለሰላም ማስገዛት እንዳለበት ያስገነዝበናል፤ በእርግጥም ለሰው ከሰላም የበለጠ አስፈላጊ ነገር የለምና ለሰላም መገዛት ተገቢ ነው፡፡

ሰው ከሰላም ተጠቃሚ እንጂ ተጐጂ የሆነበት ጊዜም፣ ቦታም የለም፤ የሰላም ክፍተት ከተፈጠረ ጣልቃ ገቢው ብዙ ከመሆኑ አንጻር ሕይወት ይጠፋል፤ ሀብት፣ ንብረት ይወድማል፤ ልማት ይቆማል፤ ድህነት ይስፋፋል፤ መጨረሻው እልቂት ይሆናል፡፡

ታዲያ ይህ እንዳይሆን ሰው ሁሉ ለራሱና ለሀገሩ ሲል የሰላም ተገዢ መሆን ይኖርበታል፡፡ ሰላም እንደ ተራ ነገር የምትታይ አይደለችምና በአፋችን ብቻ ሳይሆን በልባችን ውስጥ፣ በጥገኝነት ሳይሆን በገዢነት እንድንቀበላት በጌታችን በአምላካችንና በመድኃታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ተሰጥታናለች፤ ከዚያ አኳያ ቤተ ክርስቲያናችን በሰላም ላይ ያላት አቋም የማይናወጥ ነው፡፡

ቤተ ክርስቲያናችን በታሪኳ የፈጸመቻቸው፣ እየፈጸመቻቸው ያሉትና ለወደፊትም የምትፈጽማቸው ሁሉ የመጨረሻ ግባቸው ሰላም ነው፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሀገር መሥራች፣ የኢትዮጵያ ሕዝብ እናት፣ እንመሆኗ መጠን የሰላም፣ የፍቅር፣ የሕዝቦች አንድነትና ነጻነት ጠበቃ ሆና የኖረች ቤተ ክርስቲያን እንደሆነች ማንም የማይስተው ሐቅ ነው፡፡

ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያናችን ይህንን ሃይማኖታዊ፣ ሕዝባዊና ሀገራዊ ኃላፊነት በብቃት ስትወጣ ሕገ እግዚአብሔርን ማእከል አድርጋ በምትሠራው ሥራ የአማኙን ቀልብ በከፍተኛ ደረጃ በመሳብ እንደሆነም ይታወቃል፡፡

ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ከውጭ የሚመጣ ወራሪ ኃይል ሲያጋጥም በጸሎትና በምህላ እጆችዋን ወደ እግዚአብሔር ከመዘርጋት ጋር ታቦቷን፣ መስቀሏንና ሥዕሏን ይዛ፣ ከሕዝቡ ጋር በግንባር ተገኝታ ስለ ሃይማኖት ህልውና፣ ስለ ሕዝብ ክብርና ስለ ሀገር ልዕልና መሥዋዕት ስትከፍል የቆየች አሁንም ያለችና ለወደፊትም የምትኖር ናት፡፡

በአንጻሩ ደግሞ በሀገር ውስጥ አለመግባባት ሲፈጠር አንዱን ካንዱ ሳትለይና ሌላውን ሳታገል ሁሉንም በእኩልነትና በልጅነት መንፈስ በማየት ስትመክር፣ ስታስተምርና ስታስማማ የነበረች፣ አሁንም ያለች፣ ለወደፊትም የምትኖር የቁርጥ ቀን እናት ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡

የሀገራችን ሕዝቦች በሚያስደንቅ ሁኔታ አንድነታቸውንና ነጻነታቸውን፣ ወንድማማችነታቸውንና ፍቅራቸውን ጠብቀው ለሦስት ሺሕ ዘመናት ሊዘልቁ የቻሉት በቤተ ክርስቲያናችን ሃይማኖታዊ ሰላማዊ አስተምህሮ እንደሆነ የማይካድ ሐቅ ነው፡፡

የተወደዳችሁ ኢትዮጵያውያን ልጆቻችን !!

ከጥንት ጀምሮ ተጠብቆየኖረ የሕዝባችን ተከባብሮ፣ ተስማምቶና ተሳስቦ የመኖር ሃይማኖታዊ ባህላችን በተከበረ ቁጥር፣ ደማቅ የሆነና ዘመናትን ተሻጋሪ የሆነ ታሪክ ለመሥራት የተመቻቸ ዕድል እንደሚፈጥርልን የዘመናችን ልዩ ገጸ በረከት የሆነው ታላቁ የሕዳሴ ግድብ እና በዓለም የተመሰከረው ኢኮኖሚያዊ እድገታችን ማስረጃ ነው ፤ በታሪክ እጅግ በጣም ጉልህና ደማቅ ታሪክ ሆኖ የሚመዘገበው የዓባይ ታላቁ የሕዳሴ ግድብ የሕዝባችን የሰላምና የወንድማማችነት ፣ የፍቅርና የስምምነት ውጤት መሆኑን ልንዘነጋው አይገባም፡፡

ሀገራችን ጥንታዊትና ታላቅ ብትሆንም በመካከል ባጋጠመን የኢኮኖሚ እጥረት ምክንያት ፣ የድህነት መጣቀሻ እስከመሆን የደረስንበትን ክሥተት ለመለወጥ የሀገራችን ሕዝቦች ዳር እስከ ዳር ደፋ ቀና በሚሉበት በአሁኑ ጊዜ አልፎ አልፎ እየታዩ ያሉ ግጭቶች ቤተ ክርስቲያንን እያሳሰቧት ነው፡፡

ችግሩም እየታየ ያለው በልጆቿ መካከል በተፈጠረው ውዝግብ በመሆኑ ጉዳዩ አላስፈላጊ ከመሆኑም ሌላ የሚፈጥረው ጠባሳም በቀላሉ የሚታይ አይደለም፡፡

በዚህም ምክንያት በተፈጠረው አለመረጋጋት የልጆቻችን ሕይወት ማለፉን ፤ እንደዚሁም የብዙ ዜጎች ንብረት ፣ ሀብትና ቤት ለውድመት መዳረጉን ቤተ ክርስቲያናችን ስትሰማ ሁኔታው በእጅጉ አሳዝኖአታል፡፡

ችግሩ ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ በወንድማማችነታቸው ነቅ ታይቶባቸው በማይታወቁ ኢትዮጵያውያን ልጆቿ መካከል በመከሠቱም የቤተ ክርስቲያናችንን ኀዘን ከፍ እንዲል አድርጎታል፡፡

በመሆኑም ይህ ውዝግብ በዚህ ዓይነት ቀጥሎ የልጆቻችን ሕይወት ጥበቃና የዜጎቻችን በሰላም ሠርቶ የመኖር ዋስትና ተቃውሶ ከዚህ የባሰ እክል እንዳያጋጥም፣ እንደዚሁም እየተካሄደ ያለው የልማት መርሐ ግብር እንዳይደናቀፍ በማሰብ ቤተ ክርስቲያናችን ባላት የእናትነት ኃላፊነት የሚከተለውን መግለጫ አውጥታለች፡-

  1. ቤተ ክርስቲያናችን ‹‹ይጥዕመኒ ስማ ለሰላም›› ማለትም ‹‹የሰላም ስሟ ሁልጊዜም ይጥመኛል›› እያለች ስለ ሰላም ጥቅም ብቻ ሳይሆን ስለ ሰላም ስም ተወዳጅነት ጭምር ዘወትር የምትዘምርና የምትጸልይ ናትና አሁን ተከሥቶ ያለው ውዝግብና ተሐውኮ ቆሞ ችግሮች ሁሉ በሕጋዊ መንገድ፣ በወንድማማችነት መንፈስና በውይይት ይፈቱ ዘንድ በዚህ በያዝነው የጾም ሱባኤ በሁሉም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት ጸሎተ ምህላና የሰላም ትምህርት ተጠናክሮ እንዲካሄድ፤
  1. በየአካባቢው የሚገኙ አዛውንቶችና ሽማግሌዎች፣ ምሁራንና አባወራዎች እንዲሁም እማወራዎች ልጆቻቸውንና የአካባቢው ወጣቶችን በመምከርና በማስተማር የሰው ሕይወትን ከጥፋት፣ የሀገር ሀብትን ከውድመት እንዲታደጉ ቤተ ክርስቲያናችን ጥሪዋን ታስተላልፋለች፤
  1. ሁሉም ወገኖች አለን የሚሉትን ጥያቄ በሰላማዊ መንገድ ለሚመለከተው አካል በማቅረብ፣በውይይትና በምክክር እንዲሁም በሰላማዊና ሕጋዊ መንገድ በመጓዝ ችግሩንለመፍታት በሚደረገው ጥረት የበኩላቸውን ያደርጉ ዘንድ ቤተ ክርስቲያናችን ታሳስባለች፡፡
  1. በተፈጠረው ዉዝግብ ሕይወታቸውንና ሀብት ንብረታቸውን ላጡ ልጆቻችንና ዜጎቻችን ቤተ ክርስቲያናችን ጥልቅ የሆነ ኃዘኗን ትገልጻለች፤ በዚህም ሕይወታቸውን ያጡትን ወገኖች እግዚአብሔር በመንግሥቱ እንዲቀበልልን ቤተሰቦቻቸውንም እንዲያጽናናልን እግዚአብሔርን እንለምነዋለን፤ ለወደፊትም እንደዚህ ዓይነቱ ያለአስፈላጊ ጉዳት እንዳይደርስ ተግተን እንጸልያለን፡፡
  1. ቅዱስ መጽሐፍ ‹‹እግዚአብሔርን በመምሰልና በጭምትነት ሁሉ ጸጥ እና ዝግ ብለን እንድንኖር ልመናና ጸሎት ምልጃና ምስጋናም ስለሰዎች ሁሉ፣ ስለ ነገሥታትና ስለ መኳንንትም ሁሉ እንዲደረጉ ከሁሉ በፊት እመክራለሁ፤ ሰዎች ሁሉ ሊድኑና እውነቱን ወደማወቅ ሊደርሱ በሚወድ በመድኃኒታችን በእግዚአብሔር ፊት መልምና ደስ የሚያሰኝ ይህ ነው›› (1ጢሞ2፡1-3) ብሎ እንደሚያስተምረን የሀገራችንና የሕዝባችን ሰላምና ፀጥታ ተጠብቆ ይቀጥል ዘንድ በየሀገረ ስብከቱ ያላችሁ ሊቃነ ጳጳሳት፣ በየገዳማቱ የምትገኙ አበው መነኮሳት፣ መምህራንና ሰባክያነ ወንጌል በየዐውደ ምሕረቱ የሰላምና የፍቅር፣ የአንድነትና የስምምነት ትምህርትና መልእክት በማስተላለፍ ሕዝቡን ከጉዳትና ከመቃቃር ትጠብቁ ዘንድ ቤተ ክርስቲያናችን የሰላም ጥሪዋን አደራ ጭምር ታስተላልፋለች፡፡

እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ይባርክ

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

አባ ማትያስ ቀዳማዊ

ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

ነሐሴ 3 ቀን 2008 ዓ.ም

አዲስ አበባ ኢትዮጵያ

ጾመ ፍልሰታ ለማርያም

 ነሐሴ ፫ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው  

በነገረ ማርያም ተጽፎ እንደምናገኘው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ጥር ፳፩ ቀን በ፵፱ ዓ.ም ከዚህ ዓለም ድካም ባረፈች ጊዜ ቅዱሳን ሐዋርያት ሊቀብሯት ወደ ጌቴሴማኒ ይዘዋት ሲሔዱ አይሁድ “እንደ ልጇ ተነሣች፤ ዐረገች እያሉ እንዳያውኩን በእሳት እናቃጥላት” ብለው በዓመፃ ተነሡ፡፡ ታውፋንያ የሚባል አይሁዳዊም አጎበሩን ይዞ ሊያወርዳት ሲል የእግዚአብሔር መልአክ ሁለት እጆቹን ቀጥቶታል፡፡ ከዚህ በኋላ እግዚአብሔር አምላክ ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስን ጨምሮ እመቤታችንን በደመና ነጥቆ ወደ ገነት ወስዶ ከዕፀ ሕይወት ሥር አስቀመጣት፡፡

 

ቅዱሳን ሐዋርያትም እመቤታችን ያለችበት ቦታ እንዲገለጥላቸው ባረፈች በስምንተኛው ወር ከነሐሴ ፩ ቀን ጀምረው ሱባዔ ገብተው እግዚአብሔርን በጸሎት መጠየቅ ጀመሩ፡፡ ከዚህ ላይ “ስምንት ወር ሙሉ ምን ይዘው ቆይተው ነሐሴ ላይ ሱባዔ ገቡ?” የሚል ጥያቄ ሊነሣ ይችላል፡፡ በእውነቱ ቅዱሳን ሐዋርያት ከስብከተ ወንጌል፣ ከጾም፣ ከጸሎት፣ ከገቢረ ተአምራት፣ ተለይተው እንደማያውቁ መንፈሳዊ ሕይወታቸው ምስክር ነው፡፡

 

በመኾኑም እመቤታችን ካረፈችበት ቀን ከጥር ወር ጀምሮ እስከ ነሐሴ ድረስ ጥያቄያቸውንና ጸሎታቸውን ባያቋርጡም ከሰው ተለይተው ሱባዔ ገብተው ጾም ጸሎት የጀመሩት ግን ከነሐሴ ፩ ቀን ጀምረው ነው፡፡ ቀድሞስ የክብር ባለቤት የጌታችን የመድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደቀ መዛሙርት ኾነው እናቱ ቅድስት ድንግል ማርያም ተሠውራባቸው እንዴት ዝም ብለው ይቀመጣሉ?

 

ሁለት ሱባዔ ካደረሱ በኋላም የነገሩትን የማይረሳ፣ የለመኑትን የማይነሳ እግዚአብሔር አምላካችን ጸሎታቸውን ሰምቶ ነሐሴ ፲፭ ቀን የእመቤታችንን ሥጋ ሰጥቷቸው በክብር ገንዘው በጌቴሴማኒ ቀብረዋታል፡፡ በሦስተኛው ቀንም እንደ ልጇ እንደ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይታ ተነሥታለች፡፡ “ከመ ትንሣኤ ወልዳ፤ እንደ ልጇ ትንሣኤ” ያሰኘውም ይህ ታሪክ ነው፡፡

 

ሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ ሲሰብክ ቆይቶ ደመና ጠቅሶ ከሀገረ ስብከቱ ወደ ኢየሩሳሌም ሲመጣ እመቤታችን ከሙታን ተለይታ ተነሥታ ወደ ሰማይ ስታርግ አገኛት፡፡ በዚህ ጊዜ “ቀድሞ የልጅሽን ትንሣኤ፤ ዛሬ ደግሞ ያንቺን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁን?” ብሎ ትንሣኤዋን ባለማየቱ ኀዘን ስለ ተሰማው ከደመናው ይወድቅ ዘንድ ወደደ፡፡ “ወፈቀደ ይደቅ እምደመናሁ” እንዲል፡፡ እመቤታችንም “አይዞህ አትዘን፤ ባልነጀሮችህ ሐዋርያት ያላዩትን ትንሣኤዬን አንተ አይተሃል” ብላ ከሙታን ተለይታ መነሣቷንና ማረጓን እንዲነግራቸው አዝዛ የያዘቸውን ሰበን ሰጥታ ሰደደችው፡፡

 

እርሱም ትእዛዟን ተቀብሎ በክብር ከተሰናበታት በኋላ ወደ ሐዋርያት ሔዶ እንዳልሰማ እንዳላየ መስሎ “የእመቤታችን ነገር እንደምን ኾነ?” አላቸው፡፡ እነርሱም “አግኝተን ቀበርናት” ሲሉት “ሞት በጥር በነሐሴ መቃብር እንዴት ይኾናል?” አላቸው፡፡  በዚህ ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ ከዚህ በፊት የክርስቶስን ትንሣኤ መጠራጠሩን ጠቅሶ እየገሠፀ ስለ እመቤታችን መቀበር እነርሱ የሚነግሩትን ኹሉ መቀበል እንደሚገባው ለቅዱስ ቶማስ አስረዳው፡፡ ቅዱስ ቶማስም የያዘውን ያውቃልና ጸጥ ብሎ ሲሰማው ቆየ፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም ተቈጥቶ የእመቤታችንን ክቡር ሥጋ ለቅዱስ ቶማስ ለማሳየት ሔዶ መቃብሯን ቢከፍት የእመቤታችንን ሥጋ ሊያገኘው አልቻለም፡፡ በዚህ ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ ደንግጦ ቆመ፡፡

 

ቅዱስ ቶማስም “አታምኑኝም ብዬ ነው እንጂ እመቤታችንስ ከሙታን ተለይታ ተነሥታ ስታርግ አግኝቻታለሁ” ብሎ የሰጠችውን ሰበን ለሐዋርያት ሰጥቷቸዋል፡፡ እነርሱም በእመቤታችን ትንሣኤና ዕርገት እየተደሰቱ ሰበኑን ለበረከት ተካፍለውታል፡፡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እንደሚያስተምሩን በቅዳሴ ጊዜ ሠራዒ ዲያቆኑ በሚይዘው መስቀል ላይ የሚታሠረው መቀነት መሰል ልብስ፤ እንደዚሁም አባቶች ካህናት በመስቀላቸው ላይ የሚያደርጉት ቀጭን ልብስና በራሳቸው የሚጠመጥሙት ነጭ ሻሽ የእመቤታችን ሰበን ምሳሌ ነው፡፡

 

በዓመቱ ቅዱሳን ሐዋርያት “ቶማስ የእመቤታችን ትንሣኤዋንና ዕርገቷን አይቶ እኛ እንዴት ሳናይ እንቀራለን?” ብለው ከየሀገረ ስብከታቸው ተሰባስበው ጌታችን ሥጋዋን እንዲሰጣቸው በጠየቁበት በዚሁ ወቅት ከነሐሴ ፩ ቀን ጀምረው ሱባዔ ቢይዙ ጌታችን ልመናቸውን ተቀብሎ ነሐሴ ፲፮ ቀን እመቤታችንን መንበር፤ ጴጥሮስን ተራዳኢ ካህን፤ እስጢፋኖስን ሠራዒ ዲያቆን አድርጎ ቀድሶ እመቤታችንንም ሐዋርያትንም አቍርቧቸዋል፡፡ እነርሱም እመቤታችንን በዓይናቸው ከማየት ባሻገር አብረው ሥጋውን ደሙን ተቀብለዋል /ትርጓሜ ውዳሴ ማርያም/፡፡

 

ይህንን ትምህርት መሠረት በማድረግ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ከነሐሴ ፩-፲፭ ያለው ሁለት ሱባዔ ከሰባቱ አጽዋማት አንዱ ኾኖ በምእመናን ዘንድ መጾም እንደሚገባው ሥርዓት ሠርተውልናል /ፍት.ነገ.አን.፲፭/፡፡ ይህ ጾምም “ጾመ ማርያም (የማርያም ጾም)” ወይም “ጾመ ፍልሰታ ለማርያም (የማርያም የፍልሰቷ ጾም)” እየተባለ ይጠራል፡፡ ‹ፍልሰት› የሚለው ቃልም “ፈለሰ ሔደ፤ ተሰደደ” ካለው የግእዝ ግስ የተገኘ ሲኾን ትርጕሙም ከአንድ አገር ወደ ሌላ አገር መሔድን ያመለክታል፡፡ ‹ፍልሰታ ለማርያም› ሲልም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ካረፈች በኋላ ከጌቴሴማኒ ወደ ገነት መወሰዷን የሚያስረዳ መልእክት አለው፡፡

 

በጾመ ፍልሰታ በቤተ ክርስቲያናችን በየቀኑ በማኅሌቱ፣ በሰዓታቱና በቅዳሴው በሚደርሰው ቃለ እግዚአብሔር ነገረ ማርያም ማለትም የእመቤታችን ከመፀነሷ ጀምሮ እስከ ዕርገቷ ድረስ ያለው ታሪኳ፣ ለአምላክ ማደሪያነት መመረጧ፣ ንጽሕናዋ፣ ቅድስናዋ፣ ክብሯ፣ ርኅርራኄዋ፣ ደግነቷ፣ አማላጅነቷ፣ ሰውን ወዳድነቷ በስፋት ይነገራል፡፡ እመቤታችንን ከሚያወድሱ ድርሳናት መካከልም በተለይ ምሥጢረ ሥላሴን፣ ምሥጢረ ሥጋዌንና ነገረ ድኅነትን ከነገረ ማርያም ጋር በማዛመድ የሚያትተው ቅዳሴ ማርያም፤ እንደዚሁም ነገረ ድኅነትን ከምሥጢረ ሥጋዌ (ከነገረ ክርስቶስ) እና ከነገረ ማርያም ጋር በማመሣጠር የሚያትተው ውዳሴ ማርያምም በስፋት ይጸለያል፤ ይቀደሳል፤ ይተረጐማል፡፡ በሰንበታት የሚዘመሩ መዝሙራት፤ በየዕለቱ በቅዳሴ ጊዜ የሚነበቡ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ለተዋሕዶ በእግዚአብሔር መመረጧን፣ ዘለዓለማዊ ድንግልናዋን፣ ክብሯን፣ ቅድስናዋን፣ ንጽሕናዋን የሚያወሱ ናቸው፡፡

 

በጾመ ፍልሰታ ባሕታውያን ብቻ ሳይኾኑ ዓለማውያንም በእግዚአብሔር ቸርነት፣ በእመቤታችን አማላጅነት የሰይጣንን ፈተና ድል ለማድረግ እንዲቻላቸው ከቤተሰቦቻቸው ተለይተው በየገዳማቱና በየአብያተ ክርስቲያናቱ በዓት አዘጋጅተው፣ ሱባዔ ገብተው፣ ፈቃደ ሥጋቸውን ለፈቃደ ነፍሳቸው አስገዝተው ይጾማሉ፤ ይጸልያሉ፡፡ እንደዚሁም ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን ይቀበላሉ፡፡ እኛም የእመቤታችንን ዕረፍትና ትንሣኤ በማሰብ ከልጇ ከወዳጇ የሚገኘውን ጸጋና በረከት ተስፋ በማድረግ የአባቶቻችንንና የእናቶቻችንን ፈለግ ተከትለን በየዓመቱ ጾመ ፍልሰታን እንጾማለን፤ የምንችል ደግሞ አስቀድሰን ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን እንቀበላለን፡፡ በተጨማሪም ይህ ጾም ለእመቤታችን ያለንን ፍቅርም የምንገልጽበት ወቅት ነው፡፡ በተለይ ኦርቶዶክሳውያን ሕፃናት በአብዛኛው ትምህርተ ወንጌል የሚማሩት፤ ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን የሚቀበሉት በዚህ በጾመ ፍልሰታ ነው፡፡

 

ኹላችንም ጌታችን በስሙ ሁለትም ሦስትም ኾነን ለጸሎትና ለመልካም ሥራ ብንሰባሰብ እርሱ በመካከላችን እንደሚገኝ የገባልንን ቃል ኪዳን መሠረት በማድረግ /ማቴ.፲፰፥፳/ በጾመ ፍልሰታ ሳምንታት በጌታችን፣ በእመቤታችንና በቅዱሳን ሐዋርያት ስም በቤተ ክርስቲያን ተሰባስበን ቅዱሳት መጻሕፍትን ከመማር ባሻገር ብንጾም፣ ብንጸልይ፣ ብናስቀድስ፤ እንደዚሁም ሥጋውን ደሙን ብንቀበል በበረከት ላይ በረከትን፤ በጸጋ ላይ ጸጋን እናገኛለን፡፡ በኋላም ሰማያዊውን የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ እንችላለን፡፡

 

ነገር ግን በሕግ የተከለከለ እስኪመስል ድረስ በዚህ ወቅትም ኾነ በሌላ ጊዜ ሥጋውን ደሙን የሚቀበሉ ወጣቶች ጥቂቶች ናቸው፡፡ ስለዚህም አረጋውያንና ሕፃናት ብቻ ሳይኾኑ ወጣቶችም ጭምር የመቍረብና የመዳን ክርስቲያናዊ መብት እንዳለን በመረዳት ራሳችንን ገዝተን፣ ንስሐ ገብተን፣ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን መቀበል ይገባናል፡፡ አምላካችን በማይታበል ቃሉ “ሥጋዬን የሚበላ፤ ደሜንም የሚጠጣ የዘለዓለም ሕይወት አለው” በማለት ተናግሯልና /ዮሐ.፮፥፶፬/፡፡

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይኹን፡፡ የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት፣ የቅዱሳን ሐዋርያት ጸጋና በረከት አይለየን፡፡

ቅዱስ ፓትርያኩ ጾመ ማርያምን በማስመልከት ቃለ ምዕዳን ሰጡ

ሐምሌ ፳፰ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

Publication1

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ጾመ ማርያምን በማስመልከት ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፤ የጠቅላይ ቤተ ክህነት፣ የማኅበረ ቅዱሳን፣ የመንግሥትና የግል መገናኛ ብዙኃን ጋዜጠኞች በተገኙበት ሐምሌ ፳፰ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በመላው ዓለም ለሚገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናን ቃለ ምዕዳን ሰጥተዋል፡፡ የቅዱስ ፓትርያርኩን ሙሉ ቃለ ምዕዳንም እንደሚከተለው አቅርበነዋል፤

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን

በሀገር ውስጥም ሆነ በተለያዩ ክፍለ ዓለማት የምትገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናን ወምእመናት፣ እንኳን ለሁለት ሺሕ ስምንት መቶ ዓመተ ምሕረት የቅድስት ድንግል ማርያም ጾመ ፍልሰታ በሰላም አደረሳችሁ !!

 

‹‹ቃለ እግዚአብሔር ንጹሕ ወያሐዩ ለዓለም፤ የእግዚአብሔር ቃል ንጹሕ ነው፤ ለዘላለሙም ያድናል›› (መዝ.18፡9)፡፡

ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት ስለቃለ እግዚአብሔር አስመልክቶ በዘመረው መዝሙር ሲናገር ‹‹የእግዚብሔር ቃል ንጹሕ ነው›› ይላል፤ በእርግጥም የእግዚአብሔር ቃል የተለያዩ ፍጡራን ከሚናገሩዋቸው ቃልት ልዩ፤ ንጹሕ፤ ቅዱስና ክቡር ነው፡፡

 

የፍጡራን ቃል ከሐሰት፤ ከወላዋይነት፤ ካላዋቂነት፤ ከጥርጣሬ፤ ከአስመሳይነት፤ ከአታላይነትና ከዓቅም ውሱንነት ጋር ተቀላቅሎ ስለሚነገር ንጹሕ ነው ብሎ መናገር አይቻልም፤ የእግዚአብሔር ቃል ግን ከዚህ ሁሉ የተለየ በመሆኑ ፍጹም ንጹሕ ነው፤ እውነትም ነው፤ የእግዚአብሔር ቃል ንጹሕ ብቻ ሳይሆን ኃያልም ነውና በተናገረው መሠረት ከሚፈጸም በቀር ፍጹም የማይቀለበስ ነው፡፡

 

‹‹የእግዚአብሔር ቃል ከሚወድቅ፤ ሰማይና ምድር ቢያልፍ ይቀላል›› የሚለው የጌታችን የአምላካችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ኃይለ ትምህርት፣ የእግዚአብሔር ቃል ከሁሉም በላይ የሆነ ክብር፣ ኃይልና ጽናት ያለው መሆኑን ያስገነዝበናል፡፡ በመሆኑም ንጹሕና እውነት የሆነውን የእግዚአብሔር ቃል በማጣመም፤ ወይም በመሸራረፍ፤ ወይም በመቀናነስ ወይም ለራስ ፍላጎት በሚያመች ሁኔታ እያዛቡ መናገርና ማስተማር በእግዚአብሔር መንግሥት ከሁሉ ይልቅ ታናሽ የሚያደርግ መሆኑ በቅዱስ ወንጌል ተጽፎአል፤ (ማቴ.5፡19)፡፡

 

የእግዚአብሔር ቃል እውነተኛና ንጹሕ የመሆኑን ያህል ሕያውና ዘለዓለማዊ ነው፤ በሁለት ወገን ስለት ካለው ሰይፍም ይልቅ የሚቆርጥና የሚለይ ኃይል አለው፤ (ዕብ.4$12)፡፡ ይህም ማለት የእግዚአብሔርን ቃል እንዳለ ተቀብለው የሚጠብቁትንና የሚታዘዙለትን ለዘለዓለሙ ሕያዋን የማድረጉን ያህል፣ የሚሸራርፉትንና የሚያጣምሙትን ደግሞ የመቅጣት ሥልጣን ያለው መሆኑን ያሳየናል፡፡ በመሆኑም የሰው ልጅ ድኅነት፤ ቃሉን በመጠበቅና ባለመጠበቅ ሚዛን ላይ ተቀምጦ እንዳለ መገንዘብ አለብን፡፡

 

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት !!

ንጹሕና ሕያው የሆነው፣ ሰዎችንም ለዘለዓለሙ በሕይወት እንዲኖሩ የሚያደርገው የእግዚአብሔር ቃል፣ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን በተመለከተ የተናገረው እውነት አለ፤ በቀጣዮቹ ሁለት ሱባኤያት የቅድስት ድንግል ማርያምን ነገረ ፍልሰት ምክንያት በማድረግ የምንፈጽመው አምልኮተ እግዚአብሔር፤ የእግዚአብሔር ቃል ስለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የተናገረውን በማስታወስና ለቃሉ ተገዥ በመሆን ነው፤ የእግዚአብሔር ቃል ስለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ብዙ ተናግሮአል፤ ከተናገራቸውም መካከል፡-

  • ጸጋን የተሞላሽ ሆይ ደስ ይበልሽ፤
  • እግዚአብሔር ካንቺ ጋር ነው፤
  • ከሴቶች መካከል የተባረክሽ ነሽ፤
  • በእግዚአብሔር ፊት ጸጋን አግኝተሻል፤
  • መንፈስ ቅዱስ በአንቺ ላይ ይመጣል፤ የልዑልም ኃይል ይፀልልሻል፣
  • የጌታዬ እናት ወደኔ ትመጣ ዘንድ እኔ ማነኝ?
  • ብፅዕት ነሽ፤ ትውልድ ሁሉ ብፅዕት ይሉኛል፣
  • እነሆ ልጅሽ እነኋት እናትህ፤ የሚሉ ይገኙባቸዋል፡፡

ስለሆነም እግዚአብሔር ስለ ቅድስት ድንግል ማርያም የተናገረውን ቃል ጠቅለል አድርገን ስንመለከት በዋናነት የሚያሳየው ቅድስት ድንግል ማርያምን የጌታ እናት መሆኗን አምነው በመቀበል ‹‹ትውልድ ሁሉ ብፅዕት ነሽ›› እያሉ እንዲያከብሯት በእግዚአብሔር መታዘዙ ነው፤ ምክንያቱም የድንግል ማርያም ክብር፣ ከእግዚአብሔር ክብር ጋር የተያያዘ ባህርይ አለውና ነው፤ ቅድስት ድንግል ማርያም ምልእተ ጸጋ፤ ሙኃዘ ፍሥሐ፣ ምልእተ በረከት፤ የእግዚአብሔር ባለሟል፤ የመንፈስ ቅዱስ ማደሪያ፤ ከእግዚአብሔር ጋር ያለች፤ ብፅዕት፤ ባትሆን ኖሮ ጌታን ለመውለድ የሚያስችል ንጽሕናና ቅድስና አይኖራትም ነበር፤ እግዚአብሔር ንጹሐ ባህርይ እንደ መሆኑ መጠን በንጹሐንና በቅዱሳን አድሮ ይኖራልና፡፡

 

ቅድስት ድንግል ማርያም ጸጋን፤ በረከትን፤ ባለሟልነትን፤ የመንፈስ ቅዱስ ማደሪያ መሆንን፤ በድንግልና መፅነስን በእግዚአብሔር ኃይል መከለልን ገንዘብ አድርጋ መገኘቷ፤ ከእርስዋ የተወለደው ማን እንደሆነ በትክክል እንድናውቅ ያስችለናል፡፡

 

ቅድስት ድንግል ማርያምን ወላዲተ አምላክ ሳንል፤ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን አምላክ ወሰብእ ወሰብእ ብለን ማመንና መዳን አንችልም፤ ቅድስት ድንግል ማርያምን ምልእተ ጸጋ፣ ምልእተ በረከት፤ ሙኃዝ ፍሥሐ፤ ብፅዕት፤ ንጹሕት፤ ቅድስት ስንል ነው ከእርስዋ የተወለደውን ጌታ የባህርይ አምላክ ነው ማለት የምንችለው፣ ምክንያቱም የቅድስት ድንግል ማርያም ልዩ ጸጋና ቅድስና ለጌታችንና ለመድኃኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ማንነት አስረጅ በመሆኑ ‹‹ትውልድ ሁሉ ብፅዕት ነሽ›› እያልን እመቤታችንን እንድናከብር የእግዚአብሔር ቃል አዞናልና፤ (ሉቃ 1፡45-48)፡፡

 

ጌታችንና አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በእርሱና በቅድስት ድንግል ማርያም ያለው ግንኙነት የእናትነትና የልጅነት እነደሆነ ሁሉ በምእመናንና በድንግል ማርያም መካከል ያለው ግንኙነትም በእናትነትና በልጅነት ደረጃ እንዲሆን አዞአል፤ (ዮሐ 19፡26-27)፡፡

 

በሁሉም ዘንድ እንደሚታወቀው አንድን ልጅ አቅፋ፣ አዝላ፣ አጥብታ፣ መግባ፣ ንጽሕናውን ጠብቃ በእንክብካቤ የምታሳድግ እናት ታስፈልገዋለች፤ እናትም የሚያከብራትና የሚያስከብራት ልጅ ያስፈልጋታል፡፡ እንደዚሁም ሁሉ ጌታችን እመቤታችንን የምእመናን እናት እንድትሆን ሲያደርግ፣ በሥጋዊም ሆነ በመንፈሳዊ ሕይወታችን ተጎሳቁለን እንዳንጎዳ በጸሎቷ፣ በልመናዋ፣ በአማላጅነቷ እያገዘችና እየደገፈች ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ልታደርሰን ብሎ እንደሆነ ልብ ብሎ ማስተዋሉ ተገቢ ነው ፡፡

 

ምእመናንም የእመቤታችን ልጆች እንድንሆን ማድረጉ በዚህ ዓለም ስንኖር እርስዋን አክብረንና በስሟ እየተማፀን የበረከቷና የጸጋዋ  ተካፋይ እንድንሆን ብሎ እንደሆነ በውል መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ ‹‹እነኋት እናትህ›› ከተባለበት ሰዓት ጀምሮ እመቤታችንን ወስዶ በቤቱ አኑሯታል፤ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ እመቤታችን በእያንዳንዱ አማኝ ልጇ ቤት በመንፈስ እየገባች ትኖራለች፡፡

 

በዚህ የጌታችን ቃል፣ የሐዋርያት ትምህርትና ትውፊት መሠረት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናን ቤት፣ የእመቤታችን ቤት ሆኖ ይገኛል፤ ምክንያቱም በቤቱ የድንግል ማርያምን ሥዕል አስገብቶ እምዬ እናቴ፣ ብፅዕት ነሽ እያለ የማይጸልይና የማይማጸን የለምና፡፡ በዚህም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመን የሆነ ሁሉ የእግዚአብሔርን ቃል ሳይሸራርፍ፣ ሳይቀናንስና ሳያጣምም እንዳለ ተቀብሎ እየፈጸመ ይገኛል፤ ቃሉን በምልአት በመጠበቁና በመፈጸሙም እንደ ቃሉ ተስፋ ለዘለዓለም ሕያው ሆኖ ይኖራል፡፡

 

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት!

እግዚአብሔር በቅድስት ድንግል ማርያም በኩል የሰጠን ትልቁ ስጦታ ፍጹም ፍቅር ነው፤ ይኸውም በእናትና በልጅ መካከል ያለውን ፍቅር ነው፤ ያ ፍቅር ነው እስካሁን እመቤታችንና እኛን አስተሳስሮ የሚገኘው፤ ከዚህ ፍቅር ሊለዩን የሚሞክሩትን ሁሉ በእግዚአብሔር ቃል፣ በኦርቶዶክሳዊና በኢትዮጵያዊ መንፈስ ልንቋቋማቸው ይገባል፡፡ ቅድስት ድንግል ማርያምን ብፅዕት ነሽ እያለ የሚያመሰግን ሁሉ፣ እንደ ኤልሳቤጥ በመንፈስ ቅዱስ የተሞላና የእግዚአብሔርን ቃል በምልአት የያዘ መሆኑን እርግጠኛ ይሁን፡፡

 

በእኛና በቅድስት ድንግል ማርያም ያለው ፍቅር ዓቢይና ጥልቅ እንደመሆኑ መጠን፣ ስመ ማርያምን ጠርቶ ቁራሽ እንጀራ የሚለምን ሁሉ፣ ስለእርስዋ ፍቅር ብለን ለድሆች ስንዘክር፣ የነበረው ሃይማኖታዊ ተግባራችን ዛሬም ሳይቀዘቅዝ ሊቀጥል ይገባል፡፡

 

በዚህ በጾመ ማርያም ወቅት የተራቡትን በማጉረስ የታረዙትን በማልበስ፣ የታመሙትን በመጠየቅ፣ የታሠሩትን እግዚአብሔር ያስፈታችሁ በማለት፣ በማኅበረ ሰቡ መካከል መቻቻልን፣ መተማመንን፣ ወንድማማችነትን፣ ስምምነትን፣ ፍቅርንና ሰላምን በማስፈን ሱባኤውን ልንፈጽም ይገባል፤ ከዚህም ጋር በአሁኑ ጊዜ በስፋት እያጋጠመ ያለውን የትራፊክ አደጋ መቀነስ ይቻል ዘንድ፣ ምእመናን ሁሉ ወደ ቤተ ክርስቲያን ሲመላለሱም ሆነ በሌላ ቦታ እንቅስቃሴ ሲያደርጉ ጥንቃቄ ባልተለየው ሁኔታ እንዲሆን፣ ሹፌሮችም ሲያሽከረክሩ ኃላፊነት፣ ጥንቃቄና ማስተዋል ባልተለየው ሁኔታ እንዲሠሩ መንፈሳዊ መልእክታችንን እናስተላልፋለን፤ በየቤተ ክርስቲያኑ የሚገኙ መምህራንና ሰባክያንም የጉዳዩን አሳሳቢነት በማስገንዘብ ሕዝቡ ከትራፊክ አደጋ ጥንቃቄ ያደርግ ዘንድ በዚሁ ሱባኤ ሰፊ ትምህርትና ምክር እንዲሰጡ አደራ ጭምር መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፡፡

 

እግዚብሔር ኢትዮጵያን ይባርክ ይቀድስ፤

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

አሜን፡፡

አባ ማትያስ ቀዳማዊ

ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

 

የሰባክያነ ወንጌል እና የግቢ ጉባኤያት ሥራ አስፈጻሚዎች ሥልጠና ተጠናቀቀ

ሐምሌ ፳፯ ቀን፣ ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

በማኅበረ ቅዱሳን ትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል በስብከተ ወንጌልና ሥልጠና ክፍል፣ እንደዚሁም በስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ መርሐ ግብር ከልዩ ልዩ ጠረፋማ አህጉረ ስብከት የተውጣጡ ከሰኔ ፳፬ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ጀምሮ ለአንድ ወር ሲሠለጥኑ የቆዩ ፻፶፪ አዳዲስ ሰባክያነ ወንጌልና የዓቅም ማጎልበቻ ሠልጠኞች ብፁዕ አቡነ ዮናስ የአፋር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤ የማኅበሩ አባላት፤ በጎ አድራጊ ምእመናንና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች  በተገኙበት ሐምሌ ፳፮ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በማኅበሩ ሕንፃ ፫ኛ ፎቅ አዳራሽ በብፁዕ አቡነ ዮናስ  ጸሎተ ቡራኬ ተመርቀዋል፡፡

 

ብፁዕነታቸው “ማዕረሩሰ ብዙኅ ወገባሩ ኅዳጥ፤ መከሩስ ብዙ ነው፤ ሠራተኞች ግን ጥቂቶች ናቸው፤” በሚል ኃይለ ቃል መነሻነት “ቅኑት እንደ ገበሬ፤ ጽሙድ እንደ በሬ ኾናችሁ እግዚአብሔርን ለማገልገል ተጠርታችኋልና ቅዱስ ጳውሎስ ‹… መልካሙን ገድል ተጋድያለሁ፤ ሩጫዬን ጨርሼአለሁ፤ ሃይማኖቴን ጠብቄአለሁ፡፡ ወደ ፊት የጽድቅ አክሊል ተዘጋጅቶልኛል …› በማለት እንደ ተናገረው በተማራችሁት ትምህርት መሠረት ወንጌልን እየተዘዋወራችሁ በመስበክ አገልግሎታችሁን በትጋት ተወጥታችሁ እናንተንም ምእመናንንም ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ለማድረስ ተፋጠኑ፤” ሲሉ ለምሩቃኑ አባታዊ ቃለ ምዕዳን ሰጥተዋል፡፡

 

የአገር ውስጥ ማእከላት ማደራጃ ማስተባበሪያ ዋና ክፍል ሓላፊ፣ የማኅበረ ቅዱሳን ምክትል ዋና ጸሐፊ አቶ ሰይፈ ዓለማየሁም ምሩቃኑን “እናንተ ለእኛ አለኝታዎቻችን ናችሁ፡፡ ችግሮችን ተቋቁማችሁ በየጠረፋማው የአገራችን ክፍል እየተዘዋወራችሁ የምትሰጡትን የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ስናስብ እንበረታለን፡፡ እናንተን የሰጠን ልዑል እግዚአብሔር የተመሰገነ ይኹን፡፡ ወደፊትም ወንጌልን በመስበክ ብዙዎች የእግዚአብሔርን መንግሥት እንዲወርሱ የማድረግ ሓላፊነታችሁን በትጋት እንድትወጡ ይኹን፤” በማለት የማኅበሩን መልእክት አስተላልፈዋል፡፡ አቶ ሰይፈ በማያያዝም የሥልጠናውን ሙሉ ወጪ በመሸፈንና በልዩ ልዩ መልኩ አስተዋጽኦ ያበረከቱ በጎ አድራጊ ምእመናንን በማኅበሩ ስም አመስግነዋል፡፡

 

“ይህ የምረቃ መርሐ ግብር አገልግሎት የምትጀምሩበትና መንፈሳዊ አደራ በመቀበል ብዙ ምእመናንን አስተምራችሁ ለማስጠመቅ ቃል የምትገቡበት ዕለት መኾኑን ተገንዝባችሁ የተቀበላችሁትን አደራ በመወጣት ሰፊ አገልግሎት ለመስጠት መትጋት ይጠበቅባችኋል” የሚል ምክር ለምሩቃኑ የለገሱት ደግሞ የትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ሓላፊው ቀሲስ ዶ/ር ደረጀ ሽፈራው ናቸው፡፡

 

ከ፬፻ ሺሕ ብር በላይ ወጪ በማድረግ ሥልጠናውን የደገፉት ስማቸው እንዲጠቀስ የማይፈልጉት በጎ አድራጊ ምእመን ደግሞ “ከኹሉም በላይ በሕይወት መስበክ ይበልጣልና ምሩቃኑ ቃለ እግዚአብሔርን ከማስተማር ባሻገር ለምእመናን መልካም አርአያ ልትኾኑ፤ በአገልግሎታችሁም ብዙ ፍሬ ልታፈሩ ይገባል” ሲሉ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡

 

እኒህ ወንድም ለዝግጅት ክፍላችን ጥያቄዎች ምላሽ ሲሰጡም ከልጅነታቸው ጀምሮ በሰንበት ት/ቤት ማደጋቸውንና ለባዕለ ጠግነት የበቁትም በእግዚአብሔር ቸርነት መኾኑን ጠቅሰው “የቤተ ክርስቲያን ትልቁ የአገልግሎት መሣሪያዋ ስብከተ ወንጌል ነው ብለን ስለምናምን እኔና ባለቤቴ ተመካክረን እግዚአብሔር ከሰጠን ብዙ ሀብት ጥቂቱን በመለገስ ለዚህ መንፈሳዊ አገልግሎት እንዲውል አድርገናል፡፡ ይህንን በማድረጋችንም ትልቅ መንፈሳዊ እርካታን አግኝተናል፡፡ ባለ ሀብት ምእመናንም በሥጋችሁም በነፍሳችሁም መንፈሳዊ በረከትን እንድታገኙ ከማኅበሩ ጋር በመኾን የቤተ ክርስቲያንን አገልግሎት በመደገፍ እንደ እኛ የድርሻችሁን እንድትወጡ፤” ብለዋል፡፡

 

ምሩቃኑ በምረቃ ሥርዓቱ ያሬዳዊ ዝማሬ አቅርበዋል፡፡ በመቀጠልም ማኅበሩ ያዘጋጀላቸውን የመጽሐፍ ቅዱስ፣ የአደራ መስቀልና የምስክር ወረቀት ስጦታ በብፁዕ አቡነ ዮናስ ቡራኬ ተቀብለዋል፡፡

 

ከምሩቃኑ መካከል ከጅንካ ሀገረ ስብከት የመጡት ዲያቆን ሀብታሙ ግዛውና ሰባኬ ወንጌል ዳንኤል ኢላ የሚገኙ ሲኾን ዲያቆን ሀብታሙ አንድ ዓይኑና አንድ ኵላሊቱ አገልግሎት አይሰጡም፡፡ አንድ እግሩም በብረት የተጠገነ ነው፡፡ በተጨማሪም የደም ግፊትና ስኳር ሕመም አለበት፡፡ ሰባኬ ወንጌል ዳንኤል ኢላ ደግሞ በተፈጥሮ የሁለቱም እግሮቹ ዕድገታቸው ያልተሟላ በመኾኑ በእጆቹና በጕልበቱ እየዳኸ ነው የሚጓዘው፡፡

 

እነዚህ ሁለቱ ሰባክያነ ወንጌል በረኀውን፣ ረኀቡንና ጥሙን ታግሠው በጠረፋማ አካባቢዎች እየተዘዋወሩ ወንጌልን በመስበክ ብዙ ሺሕ አዳዲስ አማንያንን አስጠምቀው የቤተ ክርስቲያናችን አባል ሲያደርጉ ቆይተዋል፡፡ በዓቅም ማጎልበቻ ሥልጠናውም በልዩ ልዩ ርእሰ ጉዳዮች ላይ ሰፋ ያለ ግንዛቤ መጨበጣቸውንና ባገኙት ዕውቀት በመታገዝ ከቀድሞው የበለጠ አገልግሎት ለመስጠት መነሣሣታቸውን ለዝግጅት ክፍላችን አስታውቀዋል፡፡

 

እስከ ሁለት ቀናት ድረስ የሚወስድ መንገድ እየተጓዙ እንደሚያስተምሩ የሚናገሩት ሰባክያኑ በአካባቢያቸው ያለው የመጓጓዣ ችግር ለአገልግሎታቸው መሰናክል እንደ ኾነባቸው፤ እንደዚሁም ቤተ ክርስቲያንና መጠለያ ቤት አለመኖሩ አማንያኑን እንዲበታተኑ እንዳደረጋቸው ይገልጻሉ፡፡

 

አስተያየታቸውን ሲያጠቃልሉም “በጠረፋማ አካባቢዎች የሚኖሩ ወገኖቻችን ተምረው ከተጠመቁ በኋላ ካለባቸው የካህን እጦት ባሻገር ሥጋውን ደሙን የሚቀበሉባቸው፤ ልጆቻቸውን ክርስትና የሚያስነሡባቸው ጸሎት የሚያደርሱባቸው አብያተ ክርስቲያናት ባለመታነፃቸው ተመልሰው በተኵላዎች እየተነጠቁ መኾናቸውንና በመጠለያ ችግር ምክንያት መንገላታታቸውን ግምት ውስጥ በማስገባት በመላው ዓለም የሚገኙ ምእመናን ለእነዚህ ወገኖቻችን ቤተ ክርስቲያንና መጠለያ ቤት በመሥራት፤ እንደዚሁም ለሰባክያኑ መጓጓዣ የሚኾኑ ተሸከርካሪዎችን በመግዛትየድርሻቸውን እንዲወጡ እንማጸናለን” ሲሉ ጥሪያቸውን ያስተላልፋሉ፡፡

በመጨረሻም በብፁዕ አቡነ ዮናስ ቃለ ምዕ   ዳንና ጸሎተ ቡራኬ የምረቃ ሥርዓቱ ፍጻሜ ኾኗል፡፡

 

በተያያዘ ዜና በማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤያት ማስተባበሪያና ማደራጃ ዋና ክፍል ለሁለት ሳምንታት በሥራ አመራር ያሠለጠናቸው ከልዩ ልዩ የአገር ውስጥ ግቢ ጉባኤያት የተውጣጡ ፻፱ ሥራ አስፈጻሚዎች የማኅበረ ቅዱሳን አባላትና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት ሐምሌ ፳፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በማኅበረ ቅዱሳን ሕንፃ ሦስተኛ ፎቅ አዳራሽ ተመርቀዋል፡፡

 

በመርሐ ግብሩ ላይ “የሰው ልጅ የጠፋውን ሊፈልግና ሊያድን መጥቷል” በሚል ኃይለ ቃል በአገልግሎት መትጋት እንደሚገባ የሚያስረዳ ትምህርተ ወንጌል በቀሲስ ዶክተር ሙሉጌታ ሥዩም የውጭ ማእከላት ማስተባበሪያ ዋና ክፍል ሓላፊ ተሰጥቷል፡፡ ከምሩቃኑ መካከልም ወንድሞች ዲያቆናት ያሬዳዊ ወረብና ቅኔ አቅርበዋል፡፡

 

ለምሩቃኑም “የቤተ ክርስቲያን ምሥጢራትና ሥርዓት” በሚል ርእስ የተዘጋጀው መጽሐፍ በስጦታ መልክ ተበርክቶላቸዋል፡፡

 

የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጸሐፊ አቶ ተስፋዬ ቢኾነኝ፣ የአገር ውስጥ ማእከላት ማደራጃ ማስተባበሪያ ዋና ክፍል ሓላፊ፣ የማኅበሩ ምክትል ዋና ጸሐፊ አቶ ሰይፈ ዓለማየሁና የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ምክትል የቦርድ ሰብሳቢ ወይዘሮ ዓለምፀሐይ መሠረት የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች የቤተ ክርስቲያን ተስፋዎች መኾናቸውን በመጥቀስ “ለወደፊት የማኅበሩ ሥራ አመራር ተረካቢዎች እናንተ ናችሁና በሥልጠናው ባዳበራችሁት ክህሎት በግቢ ጉባኤ ቆይታችሁም ኾነ ከግቢ ስትወጡ በማኅበሩ አገልግሎት ውስጥ በመሳተፍ የቤተ ክርስቲያንን ተልእኮ ለማስፈጸም እንድትተጉና በመንፈሳዊ ሕይወታችሁም ለወጣቱ ትውልድ አርአያ እንድትኾኑ” ሲሉ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

 

የሥልጠናው ዓላማ በማኅበረ ቅዱሳን ልዩ ልዩ መዋቅሮች ተተክተው ሊያገለግሉ የሚችሉ ሥራ አስፈጻሚዎችን ማፍራት መኾኑን ለዝግጅት ክፍላችን የገለጹት የግቢ ጉባኤያት ማስተባበሪያና ማደራጃ ዋና ክፍል ሓላፊ፣ የማኅበረ ቅዱሳን ምክትል ዋና ጸሐፊ አቶ እስጢፋኖስ ታፈሰ፤ እንደዚሁም ከ፻፱ኙ ሠልጣኞች መካከል ፲፮ቱ እኅቶች መኾናቸውን ያስታወቁት የማብቂያና ማሰማሪያ ክፍል ተጠሪው አቶ ደረሰ ታደሰ የሥልጠናው ወጪ “መሰባሰባችንን አንተው” በሚል መሪ ቃል ከታኅሣሥ ፳-፳፮ ቀን፣ ፳፻፰ ዓ.ም በተዘጋጀው የገቢ ማሰባበሰቢያ መርሐ ግብር በተገኘው ገንዘብ መሸፈኑን አስታውቀዋል፡፡

 

በተጨማሪም ለሥልጠናው መሳካት ልዩ ልዩ አስተዋጽኦ ላበረከቱ ለኤስድሮስ ኮንስትራክሽንና ንግድ አክስዮን ማኅበር፣ ለሐይመት ንግድ ሥራዎች ድርጅት፣ ለከራድዖን ካፌና ሬስቶራንት፣ ለሌሎችም በጎ አድራጊ ተቋማትና ግለሰቦች በማኅበሩና በሥልጠናው አስተባባሪ ኰሚቴ ስም ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡ ለወደፊቱ ማኅበሩ በግቢ ጉባኤያት ላይ ብዙ ሥራዎችን ለማከናወን ማቀዱን ጠቅሰው “ለዚህም የምእመናን ድጋፍ እንዳይለየን” ሲሉ ጥሪያቸውን ያስተላልፋሉ፡፡

 

በዚህ ሥልጠና የቤተ ክርስቲያንን ማንነት፣ የመንፈሳዊ ሕይወትን ትርጕም፣ ፍቅርን፣ ትሕትናን፣ ፈተናዎችን የማለፍ ጥበብንና ሌላም በርካታ ዕውቀትን እንደ ቀሰሙበት፤ እንደዚሁም የማኅበረ ቅዱሳንን ማንነት በስፋት እንደ ተረዱበትና ለወደፊቱም ቤተ ክርስቲያንን በትጋት ለማገልገል የሚያስችል ዓቅም እንዳጎለበቱበት በዕለቱ አስተያየት የሰጡት ከደብረ ማርቆስ፣ ከጎንደር፣ ከመቱ፣ ከሠመራና ከአዲስ አበባ አልካን ኪያሜድ ግቢ ጉባኤያት የመጡ ሠልጣኞች ተናግረዋል፡፡

መርሐ ግብሩም በአባቶች ጸሎት ተፈጽሟል፡፡

የቤተ ክርስቲያን ቅርሶቻችንን ከዘራፊዎች እንጠብቅ!

ሐምሌ ፳፯ ቀን፣ ፳፻፰ ዓ.ም

በይብረሁ ይጥና

book 3

ስልሳ አምስት ጥንታውያን የቤተ ክርስቲያን የብራና መጻሕፍት ሊሸጡ ሲሉ ሐምሌ ፯ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በፖሊስ ቍጥጥር ሥር መዋላቸውን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት የቅርስ ጥበቃ ቤተ መጻሕፍት ወመዘክር መምሪያ ሓላፊ አስታውቀዋል፡፡

 

የመምሪያው ሓላፊ መጋቤ ሰላም ቀሲስ ሰሎሞን ቶልቻ በተለይ ለሚድያ ክፍላችን እንዳስታወቁት፤ ልዩ ልዩ ጥንታውያን የብራና መጻሕፍት በአዲስ አበባ ቸርችል ጎዳና አካባቢ በሚገኝ የስጦታ ዕቃዎች መሸጫ ሱቅ ሊሸጡ ሲሉ በፖሊስ ቁጥጥር ሥር ሊውሉ ችለዋል፡፡

 

ኹሉም ጥንታውያን የብራና መጻሕፍት ከየት ገዳም ወይም ደብር እንደ ተዘረፉ እስከ አሁን ድረስ መረጃ ባይገኝም ከመጻሕፍቱ መካከል ሦስቱ በሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት እንደ ተጻፉ ለማወቅ መቻሉን መጋቤ ሰላም ቀሲስ ሰሎሞን ቶሎቻ ተናግረዋል፡፡

books 2

“የብራና መጻሕፍቱ ከየትና መቼ እንዲሁም በማን እንደተዘረፉ ለማወቅ ፖሊስ የምርመራ ውጤቱን እስኪያሳውቅና ወንጀለኞቹ ፍርድ እስኪያገኙ ድረስ ሕጉ በሚፈቅደው መንገድ መጻሕፍቱን ለመረከብ መምሪያው ጥረት እያደረገ ይገኛል፡፡ ቅርሶቹን በሓላፊነት ተረክበን የቅርሶቹ ባለቤት ከታወቀ በኋላ ወደየመጡበት ቦታ እንዲመለሱ፤ ባለቤታቸው ካልታወቀ ደግሞ በጠቅላይ ቤተ ክህነት ቤተ መጻሕፍት ወመዘክር እንዲቀመጡ ይደረጋል” ሲሉ የመምሪያው ሓላፊ አስገንዝበዋል፡፡

 

በመጨረሻም “ቅርሶቻችን የማንነታችን መገለጫዎችና በገንዘብ የማይተመኑ የአገራችን ሀብቶች ናቸው፡፡ አባቶቻችን እየተራቡና እየተጠሙ ጠብቀው ያቆዩልን እነዚህ ጥንታውያን ቅርሶቻችን በዘራፊዎች  ኹሉም ሰው በተለይ ወጣቱ ትውልድ ጥበቃና ክብካቤ ሊያደርግላቸው ይገባል” ሲሉ መጋቤ ሰላም ቀሲስ ሰሎሞን ቶልቻ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

book

የብራና መጻሕፍቱ ጉዳይ በአራዳ ክፍለ ከተማ የፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ክትትል እየተደረገበት ሲኾን፤ የፍርድ ቤት ውሳኔውንም እንደ ደረሰን የምናቀርብ ይኾናል፡፡