የቤተ ክርስቲያን ቅርሶቻችንን ከዘራፊዎች እንጠብቅ!

ሐምሌ ፳፯ ቀን፣ ፳፻፰ ዓ.ም

በይብረሁ ይጥና

book 3

ስልሳ አምስት ጥንታውያን የቤተ ክርስቲያን የብራና መጻሕፍት ሊሸጡ ሲሉ ሐምሌ ፯ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በፖሊስ ቍጥጥር ሥር መዋላቸውን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት የቅርስ ጥበቃ ቤተ መጻሕፍት ወመዘክር መምሪያ ሓላፊ አስታውቀዋል፡፡

 

የመምሪያው ሓላፊ መጋቤ ሰላም ቀሲስ ሰሎሞን ቶልቻ በተለይ ለሚድያ ክፍላችን እንዳስታወቁት፤ ልዩ ልዩ ጥንታውያን የብራና መጻሕፍት በአዲስ አበባ ቸርችል ጎዳና አካባቢ በሚገኝ የስጦታ ዕቃዎች መሸጫ ሱቅ ሊሸጡ ሲሉ በፖሊስ ቁጥጥር ሥር ሊውሉ ችለዋል፡፡

 

ኹሉም ጥንታውያን የብራና መጻሕፍት ከየት ገዳም ወይም ደብር እንደ ተዘረፉ እስከ አሁን ድረስ መረጃ ባይገኝም ከመጻሕፍቱ መካከል ሦስቱ በሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት እንደ ተጻፉ ለማወቅ መቻሉን መጋቤ ሰላም ቀሲስ ሰሎሞን ቶሎቻ ተናግረዋል፡፡

books 2

“የብራና መጻሕፍቱ ከየትና መቼ እንዲሁም በማን እንደተዘረፉ ለማወቅ ፖሊስ የምርመራ ውጤቱን እስኪያሳውቅና ወንጀለኞቹ ፍርድ እስኪያገኙ ድረስ ሕጉ በሚፈቅደው መንገድ መጻሕፍቱን ለመረከብ መምሪያው ጥረት እያደረገ ይገኛል፡፡ ቅርሶቹን በሓላፊነት ተረክበን የቅርሶቹ ባለቤት ከታወቀ በኋላ ወደየመጡበት ቦታ እንዲመለሱ፤ ባለቤታቸው ካልታወቀ ደግሞ በጠቅላይ ቤተ ክህነት ቤተ መጻሕፍት ወመዘክር እንዲቀመጡ ይደረጋል” ሲሉ የመምሪያው ሓላፊ አስገንዝበዋል፡፡

 

በመጨረሻም “ቅርሶቻችን የማንነታችን መገለጫዎችና በገንዘብ የማይተመኑ የአገራችን ሀብቶች ናቸው፡፡ አባቶቻችን እየተራቡና እየተጠሙ ጠብቀው ያቆዩልን እነዚህ ጥንታውያን ቅርሶቻችን በዘራፊዎች  ኹሉም ሰው በተለይ ወጣቱ ትውልድ ጥበቃና ክብካቤ ሊያደርግላቸው ይገባል” ሲሉ መጋቤ ሰላም ቀሲስ ሰሎሞን ቶልቻ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

book

የብራና መጻሕፍቱ ጉዳይ በአራዳ ክፍለ ከተማ የፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ክትትል እየተደረገበት ሲኾን፤ የፍርድ ቤት ውሳኔውንም እንደ ደረሰን የምናቀርብ ይኾናል፡፡