trinity 2

በዓለ ሥላሴ

ሐምሌ 7 ቀን 2006 ዓ.ም.

መ/ር ሳሙኤል ተስፋዬ

 trinity 2

ወበዛቲ ዕለት ቦኡ ሥሉስ ቅዱስ ውስተ ቤተ አብርሃም ወተሴሰዩ ዘአቅረቦ ሎሙ፡፡ በከመ መጽሐፍ ውስተ ኦሪት ወአብሠርዎ ልደቶ ለይስሐቅ ወባረክዎ፡፡ በዚችም ቀን ልዩ የሆኑ ሦስቱ አካላት /ቅድስት ሥላሴ/ በኦሪት መጽሐፍ እንደ ተጻፈ ወደ አብርሃም ቤት ገቡ ያቀረበላቸውንም ተመገቡ፡፡ የይስሐቅንም ልደት አበሠሩት ባረኩት አከበሩትም፡፡

መጽሐፈ ስንክሳር ዘሐምሌ ሰባት

ሥላሴ ማለት በቅዱሳት መጻሕፍት መሠረት አንድ አምላክ በሦስት አካላት እንዳለ ለአበው ለነቢያትና ለሐዋርያት መገለጡን አምነን የምንማረው ትምህርት ነው፡፡ሥላሴ ማለት የግእዝ ቃል ሲሆን ሦስት፤ ሦስትነት ማለት ነው፡፡

የአንድ አምላክ በሦስትነት መገለጥን ለመረዳት በኦሪት ዘፍጥረት 1፡26 ላይ በተገለጠው መሠረት “እግዚአብሔርም አለ ሰውን በመልካችን እንደምሳሌችን እንፍጠር” ይላል ይህ አገላለጽ “እግዚአብሔርም አለ” ሲል አንድነትን (አንድነታቸውን) “እንፍጠር” ሲል ከአንድ በላይ (ሦስትነትን) መሆንን ያስረዳል፡፡

በኦሪት ዘፍጥረት 3፡22 ላይ “አዳም ከእኛ እንደ አንዱ ሆነ” የሚለው አገላለጽ ከአንድ በላይ መሆንን የሚያስረዳ ነው፡፡በኦሪት ዘፍጥረት 11፡5-7 የተጠቀሰው “ኑ እንውረድ ቋንቋቸውን እንደባልቅ”በማለት ሥላሴ የተናገሩት ከአንድ በላይ (ሦስትነት) መሆንን የሚያመለክት ነው፡፡

በኦሪት ዘፍጥረት18 ላይ ሥላሴ ለአብርሃም እንደተገጹለት የሚያስረዳ ሀሳብ የያዘ አገላለጽ ሲሆን ሥላሴ ለአብርሃም በመገለጻቸው አብርሃም ሥላሴን በእንግድነት አሰተናግዷል፡፡የሥላሴ ባለሟል መሆኑ ተረጋግጧል፡፡ በእርግናው ጊዜ ልጅ እንደሚያገን ተበስሮለታል፡፡ ዘሩ እንደ ሰማይ ከዋክብት እንደ ምድር አሸዋ እንደሚበዛ በሥላሴ ቃል ተገብቶለታል፡፡

አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሚጠመቅበት ጊዜም የሥላሴ ምስጢር ተገልጧል፡፡ “እግዚአብሔር አብ የምወደው ልጄ ይህ ነው” ሲል እግዚአብሔር ወልድ ሲመጠቅ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ በርግብ አምሳል ተገልጧል፡፡ ማቴ.3፡13 አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያትን ሂዱና በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችሁ ደቀመዛሙርቴ አድርጉ” ማቴ. 14፡28 ሲል ሦስትነት የሚገልጽ መልእክት አስተላልፏል፡፡ እንግዲህ ሥላሴ ስንል በስም በአካል፣ በግብር የተለዩ መሆናቸውን ያስረዳል፡፡ ይኸውም፡-

የአካል ሦስትነት፡-

    • አብ የራሱ መልክ፣ ገጽ፣ አካል አለው፡፡

    • ወልድ  የራሱ መልክ፣ ገጽ፣ አካል አለው፡፡

    • መንፈስ ቅዱስ፡- የራሱ መልክ፣ ገጽ አካል አለው፡፡

የስም ሦስትነት ስንል፡- የአንዱ ስም ለአንዱ የማይሆን አብ፣ ወልድ፣ መንፈስ ቅዱስ በመባል ይጠራሉ፡፡

የግብር ሦስትነት ስንል፡- አብ ወላዲ፣ አስራጺ ሲሆን ወልድ ተወላዲ ነው የተወለደውም ከአብ ነው፡፡ መንፈስ ቅዱስ ሰራጺ ነው፡፡ የሰረጸውም ከአብ ነው፡፡

የሥላሴን አንድነትና ሦስትነት ለመረዳት በሥላሴ ፈቃድ መጻሕፍት እንዳስተማሩ ሊቃውንት እንደተረጉሙልን እንጂ ማንም በገዛ ፈቃዱ ተመራምሮ አይደርስበትም፡፡

በዓለ ሥላሴ

በዓላት የሰው ልጅ በእግዚአብሔር የተደረገለትን የቸርነት ሥራ በማሰብ ቅዱሳን ጻድቃን ሰማዕታት ያደረጉትን ተጋድሎና ተአምራት በመስማትና በማሰማት የተደረገውን ድንቅ ነገር በመዘከር በደስታ የሚከበሩ ዕለታት ናቸው፡፡ “በቃለ አሜን ወበትፍስሕት ድምፁ እለ ይገብሩ በዓለ፡- በዓለ የሚያደርጉ ሰዎች የደስታና የምስጋና ቃል አለው” እንዳለ ቅዱስ ዳዊት መዝ.41፡5 የበዓል መከበርን ያሳወቁት ሥላሴ ሲሆኑ፤ ሥላሴ ፍጥረታትን ስድስት ቀናት ፈጥረው ሰባተኛውን ቀን ቀዳሚትን አርፈውበታል፡፡ “በሰባተኛውም ቀን ከሥራው ሁሉ ዐረፈ፡፡ እግዚአብሔር ሰባተኛውን ቀን ባርከውም ቀድሰውም እግዚአብሔር ሊያደርገው ከፈጠረው ሥራ ሁሉ በእርሱ ዐርፏልና” ዘፍ.1፡1-3 እንዲል

በዚህ መሠረትነት በዓል እንዲከበር የመደቡት ሥላሴ ሲሆኑ የመጀመሪያው የሥላሴ መታሰቢያና የበዓል አከባበር መጀመሪያ የሆነችው ቀዳሚት ናት፡፡

የዛሬው ሐምሌ 7 ቀንም ሥላሴ በአብርሃም ቤት ገብተው ቸርነታቸውና ፍቅራቸውን የገለጹበት፣ አብርሃምን የባረኩትና ልጅ እንደሚወልድ፣ መጻዒው ሕይወቱን የነገሩት ዕለት ስለሆነ በዓሉን ስናዘክር ሥላሴን እናመሰግናለን፡፡ ቸርነታቸው፣ ፍቅራቸው፣ ትድግናቸው እንዳይለየን እንማጸናለን፡፡ የቅድስት ሥላሴ ቸርነት አይለየን፡፡

“ሰማዕታት የዚህችን ዓለም ጣዕም በእውነት ናቁ፤ ደማቸውን ስለ እግዚአብሔር አፈሰሱ፤ ስለ መንግሥተ ሰማያት መራራ ሞትን ታገሱ፡፡” ውዳሴ ማርያም ዘሐሙስ ቁ.6

 

ሶሪያዊው ቅዱስ ኤፍሬም በቅዱስ ዳዊት ሕይወት የተከወናውን በምሥጢር ስቦ አምጥቶ የሰማዕታትን ክብር አጎልቶ ተናግሮበታል፡፡ ታሪኩ እንዲህ ነው፡፡ ቅዱስ ዳዊትን እግዚአብሔር አምላክ ለእስራኤል አነገሠው፡፡ በዙሪያው የነበሩ ኤሎፍላዊያንን አጥፍቶ ደብረ ጽዮንን /መናገሻ ከተማውን/ አቅንቶ ሲኖር ከዕለታት አንድ ቀን ዳዊት ታመመ፡፡የዳዊትን መታመም ሰምተው፣ ካሉበት ተነስተው የዳዊትን ከተማ በተለይም ቤተልሔምን ከበቧት፡፡ ዳዊት ይህን ሰምቶ “ወይ እኔ ዳዊት! ድሮ ታመምሁና ጠላቶቼ ሰለጠኑ ሲል የኀያላኑን ልቦና ለመፈተን ከቤተልሔም ምንጭ ውኃ ማን ባመጣልኝ?” አለ፡፡ በዚህ ጊዜ የጭፍሮቹ አለቆች ሦስቱ ማለትም አዲኖን፣ ኢያቡስቴ ኤልያና ረዋታቸውን /የውኃ መያዣ/ ይዘው፣ ጦራቸውን አሰልፈው፣ ጠላቶቹን ድል ነስተው፣ ዳዊት ሊጠጣ የወደደውን ውኃ አመጡለት፡፡ቅዱስ ዳዊትም ያንን ውኃ አፈሰሰው “ለምን አፈሰስከው?” ቢሉት “ደማችሁን መጣጠት አይደለምን?” ብሎ፤ ይህም ከጽድቅ ገብቶ ተቆጠረለት፡፡ 2ሳሙ.23፥13-17

አባቶቻችን ይህንን ሲያመሰጥሩት የፍጥረት ሁሉ ቁንጮ አባታችን አዳም ከተድላ ገነት ወደ ምድረ ፋይድ፥ ከነጻነት ወደ መገዛት፥ ከልጅነት ወደ ባርነት፥ በወረደና ፍትወታት እኩያት ኀጣውእ በጠላትነት በተነሱበት ጊዜ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ከተገኘ ከጌታ ጎን የተገኘ ማየ ገቦ ይጠጣ ዘንድ ወደደ፡፡ የትሩፋት አበጋዞች ሃይማኖት፣ ተስፋ፣ ፍቅር፣ ፈጥነው ተነሱ፡፡ በአጋንንት ከተማ ተዋጉለት ይጠጣው ዘንድ የወደደውን ማየ ገቦ አመጡለት፡፡ ማለትም የአዳም ልጅነት በከበረው የክርስቶስ የደሙ ፈሳሽነት የሥጋው መሥዋዕትነት ተመለሰለት፡፡ ይህንን ለአዳምና ለልጆቹ የባህርይ አምላክ ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተቀበለውን ፀዋትወ መከራ እያሰቡ ሰማዕታት በእግዚአብሔር ፍቅር ተቃጥለው “እግዚአብሔርን ካዱ ለጣዖት ሰገዱ” ሲባሉ “እግዚአብሔርን አንክድም ለጣዖት አንሰግድም” ብለው ደማቸውን አፈሰሱ ይህም ጽድቅ ሆኖ ተቆጠረላቸው፡፡ /ውዳሴ ማርያም ትርጓሜ ዘሐሙስ/

“ሰማዕት” ማለት ምስክር ማለት ነው፡፡ ይህ ደማቸውን ስለ እግዚአብሔር ፍቅር ብሎ ማፍሰስ ጽድቅ ሆኖ ተቆጠረላቸው፥ የዳዊት ወታደሮች ስለ ዳዊት ፍቅር ብለው “ደማችን ይፍሰስ” እንዲሉ፤ ዳዊትም ያመጡለትን ውኃ መጠጣት ደማችሁን እንደመጠጣት ነው ብሎ በፍቅር ምክንያት ውኃውን እንዳፈሰሰው፥ ይህም ጽድቅ ሆኖ እንደተቆጠረለት፥ የእግዚአብሔር ወዳጆች የሆኑ ቅዱሳን ሰማዕታትም እግዚአብሔርንና የእግዚአብሔር ሃይማኖት የሆነችው እውነተኛይቱን ሃይማኖት ወደው ደማቸውን አፈሰሱ፣ አጥንታቸውን ከሰከሱ፣ ስለዚህ እንደ ፀሐይ አብርተው በሰማያት ዛሬም ስለ እኛ እየማለዱ አሉ፡፡

ከእነዚህም መካከል ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ጳውሎስ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ታስባቸዋለች፡፡ ሐምሌ 5 ሰማእትነት የተቀበሉበት ቀን መታሰቢያቸውን ታዘክራለች፡፡ ከመጽሐፈ ስንክሳር ዘርኀ ሐምሌ ዕለቱን በማስመለከት ያገኘነውን መረጃ እንዲህ ተዘጋጅቷል፡፡

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሐምሌ አምስት በዚች ቀን የክቡራንና የዐበይት አባቶቻችን ሐዋርያት የጴጥሮስና የጳውሎስ የሰማዕትነታቸው መታሰቢያ ነው፡፡ ሰላም ለከ ጴጥሮስ ተልሚድ፡፡ ዘኢያቅበጽከ ተስፋ ነገረ ኑፋቄ ወካህድ፡፡ እንዘ ትረውጽ ጥቡዐ ለመልእክተ ክርስቶስ ወልድ፡፡ አመ ለሊከ ወሬዛ ቀነትከ በእድ፡፡ ወአመ ልህቀ አቅነትከ ባዕድ፡፡

ይህም ጴጥሮስ ከቤተ ሳይዳ ነበር ዓሣ አጥማጅም ነበር ጌታችንም ከተጠመቀባት ዕለት ማግሥት አግኝቶ መረጠው፤ ከእርሱ አስቀድሞም ወንድሙ እንድርያስን አግኝቶ መረጠው፡፡ መድኃኒታችንንም እስከ መከራው ጊዜ ሲአገለግለው ኖረ፤ ፍጹም ሃይማኖት፣ ለጌታውም ቅንዓትና ፍቅር ነበረው፡፡ ስለዚህም በሐዋርያት ሁሉ ላይ አለቃ አድርጎ ሾመው፡፡

ጌታችንም ሰዎች ማን እንደሆነ ማንም እንደሚሉት ስለ ራሱ በጠየቃቸው ጊዜ ሌሎቹ ኤርምያስ ይሉሃል ወይም ኤልያስ ወይም ከነቢያት አንዱ ነው ይሉሃል አሉት፡፡ ጴጥሮስ ግን የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ አንተ ነህ አለ፡፡ ጌታችንም የሃይማኖት አለት የቤተ ክርስቲያንም መሠረት ነህ ብሎ ብፅዕና ሰጠው የመንግሥተ ሰማያትንም መክፈቻ ቁልፍ ሰጥቼሃለሁ አለው፡፡

አጽናኝ የሆነ የመንፈስ ቅዱስንም ጸጋ ከተቀበለ በኋላ ተናጋሪዎች በሆኑ በዚህ ዓለም ተኲላዎች መካከል ገባ በውስጣቸውም ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ሰበከ፤ ቊጥር የሌላቸው ብዙዎች አሕዛብንም መልሶ የዋሆች ምእመናን አደረጋቸው፡፡

ጌታችንም የማይቈጠሩ ታላላቅ ድንቆችና ተአምራቶችን በእጆቹ አደረገ፤ ጥቅም ያላቸው ሦስት መልእክቶችንም ጽፎ ለምእመናን ላካቸው፡፡ ለማርቆስም ወንጌሉን ተርጒሞ አጽፎታል፡፡ ከዚህም በኋላ ወደ ሮሜ ከተማ ገባ፤ የከተማው መኳንንት ወደሚሰበሰቡበት ወደ ታላቁ የጨዋታ ቦታም ሔዶ በታላቅ ድምፅ እንዲህ ብሎ ተናገረ የሚራሩ ብፁዓን ናቸው ለርሳቸውም ይራሩላቸዋልና የዚህንም ተከታታይ ቃሎች ተናገረ፡፡ ከዚያም ከዚያ የነበሩ አራት የደንጊያ ምሰሶዎችም በሚያስፈራ ድምፅ አሜን አሉ፤ የተሰበሰቡትም ይህን ቃል በሰሙ ጊዜ ደነገጡ፡፡ ከሰባ ዓመት ጀምሮ ሰይጣን ያደረበት አንድ ሰው ነበረ፤ ከእነዚያ ደንጋዮች ቃልን ስለ ሰማ ያን ጊዜ ጋኔኑ ጣለው ከእርሱም ወጥቶ ሔደ፡፡ መኳንንቱም ፈርተዋልና ስለዚህ ነገር እያደነቁ ወደ ቤታቸው ገቡ፡፡

ከከተማ መኳንንቶችም ቀውስጦስ የሚባል አንዱ ወደ ቤቱ በገባ ጊዜ ስሟ አክሮስያ ለምትባል ሚስቱ ዓለምን ስለ መተው ለድኆችም ስለመራራትና የመሳሰለውን ቃል ጴጠሮስ እንዴት እንዳስተማረ ነገራት፡፡ እርሷም በሰማች ጊዜ በልቧ ነቅታ ይህ ነገር መልካምና ድንቅ ነው አለች፡፡ ጴጥሮስ ያስተማረውንም ሁሉ ያደርጉ ዘንድ በአንድነት ተስማሙ ከዚህም በኋላ ገንዘባቸውን ሁሉ ለድኆች ሰጡ ከዕለት ራት በቀር ምንም አላስቀሩም፡፡ ከጥቂት ቀኖችም በኋላ ንጉሡ ስለ መንግሥት ሥራ ከርሱ ጋራ ለመማከር በቶሎ እንዲደርስ ወደርሱ መልእክትን ላከ፡፡

ቀውስጦስም ይህን በሰማ ጊዜ ገንዘብ ስላልነበረው ፈርቶ ደነገጠ ተጨነቀም፡፡ ምክንያትም አመካኝቶ ይሠወር ዘንድ ከሚስቱ ጋራ ተማከረ፡፡ እርሷ ግን ምክንያት አታድርግ ነገር ግን ወደ ንጉሡ ሒድ የጴጥሮስም አምላክ ጐዳናህን ያቅናልህ አለችው፤ እርሱም ነገርዋን ተቀብሎ ወደ ንጉሡ ሔደ፤ በመንገድም ከእግዚአብሔር የታዘዘ ብዙ በረከትን አገኘ፡፡ ወደ ንጉሡም ደረሰ፤ ንጉሡም በደስታና በክብር ተቀበለው፡፡

ከሦስት ዓመት በኋላም ወደ ቤቱ በተመለሰ ጊዜ ሁለቱ ልጆቹ የተመረዘ ውኃ ጠጥተው እነሆ ሙተው ነበር፤ ሚስቱም ለእርሱ መንገርን ፈራች ብዙ ምሳሌዎችን ከመሰለችለት በኋላ ነገረችው፡፡ በሰማ ጊዜም እጅግ አዝኖ አለቀሰ፡፡ ሚስቱም እንዲህ አለችው ጌታዬ ሆይ ልባችን የሚጽናናበትን እርሱ ያደርግልናልና የጴጥሮስን ፈጣሪ እግዚአብሔርን እንለምነው፡፡ ሊጸልዩም በጀመሩ ጊዜ ቀውስጦስና አክሮስያ ሆይ የደቀ መዝሙሬ የጴጥሮስን ቃል ስለሰማችሁና ስለተቀበላችሁት ስለዚህ ልጆቻችሁን በሕይወታቸው እሰጣችኋለሁ የሚል ቃልን ከሰማይ ሰሙ ያን ጊዜም ልጆቻቸው ድነው ተነሡ ቀውስጦስና ሚስቱም ደስ አላቸው የተመሰገነ እግዚአብሔርንም አመሰገኑት፡፡

አሊህም ከሞት የተነሡ ልጆች ለቅዱስ ጴጥሮስ ደቀ መዝሙሮቹ ሆኑ፤ የአንዱ ስሙ ቀሌምንጦስ ነው እርሱም ቅዱስ ጴጥሮስ ያየውንና ጌታችን በሥጋ ወደ ሰማይ በሚዐርግ ጊዜ የገለጠለትን ምሥጢር ሁሉ የነገረው ነው፤ ሰዎች ሊያዩአቸው የማይገባቸውን መጻሕፍትን አስረከበው፡፡ ይህንም ቀሌምንጦስን ሊቀ ጵጵስና ወንድሙን ዲቁና ሾማቸው፡ ከዚህም በኋላ ዳግመኛ ቅዱስ ጴጥሮስ አምላክን የወለደች የንጽሕት ድንግል እመቤታችን ማርያም ክብርዋን በምሳሌ አየ፡፡

በቀስት አምሳል ደመናን አይቷልና በላይዋም የብርሃን ድንኳን ነበረ በድንኳኑም ውስጥ አምላክን የወለደች ቅድስት ድንግል ማርያም ተቀምጣለች፡፡ በእጆቻቸው ውስጥ የነበልባል ጦሮችንና ሰይፎችን የያዙ መላእክትና የመላእክት አለቆች በዙሪያዋ ነበሩ፡፡ እንዲህም እያሉ ያመሰግኗት ነበር ከእርሷ የድኅነት ፍሬ የተገኘ የሠመረች የወይን ተክል አንች ነሽ፡፡ ማሕፀንሽ የእግዚአብሔርን በግ የተሸከመ ንጽሕት አዳራሽ አንቺ ነሽ፡፡

ሁለተኛም እንዲህ ይሏት ነበር፡፡ የብርሃን እናቱ ሆይ የምሕረት መገኛ ሆይ ደስ ይበልሽ የአማልክት አምላክ የፍጥረት ሁሉ ጌታ የሆነ የመድኅን ዙፋን ሆይ ደስ ይበልሽ ክብርና ምሥጋናን የተመላሽ የፍጥረት ሁሉ እመቤት ደስ ይበልሽ፡፡

መላእክትም ምሥጋናዋንና ሰላምታዋን በአደረሱ ጊዜ ክብር ምሥጋና ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለእርስዋ ተገልጦ ከእርስዋ በቀር ማንም ሊያውቀው የማይቻል ነገርን ነገራት ወዲያውኑም ምድር ተናወጸች ሊነገር የማይቻል ምሥጢራትንም ገለጠላት፡፡

ከዚህም በኋላ መድኃኒታችን በሀገሩ ሁሉ ቅዱስ ወንጌልን ይሰብክ ዘንድ ጴጥሮስን አዘዘው፡ ጴጥሮስም ወጥቶ ሔደ፤ ኢዮጴ ወደምትባል የባሕር ዳርቻና ልድያ ወደምትባል አገር ደረሰ፡፡

በአንዲት ዕለትም በኢዮጴ ሳለ ብርህት ደመና ዞረችው፡፡ እነሆም ሰፊ መጋረጃ ወደ እርሱ ወረደች፤ በውሰጥዋም የእንስሳት የምድረበዳ አውሬዎችና የሰማይ አዕዋፍ አምሳል ነበረ፡፡ ጴጥሮስ ሆይ ተነስና አርደህ ብላ የሚል ቃልም ከሰማይ ጠራው፡፡ ጴጥሮስም አቤቱ አይገባኝም ርኩስ ነገር አልበላም ወደ አፌም ከቶ አልገባም አለ፡፡

ያም ቃል ዳግመኛ ጠራውና እግዚአብሔር ንጹሕ ያደረገውን አንተ ርኩስ ነው አትበል አለው፡፡ ያም ቃል ሦስት ጊዜ መላልሶ እንዲህ ነገረው፡፡ በየንግግሩም ወደ እሪያዎች ወደ አራዊትና ወደ አዕዋፍ ስዕሎች ያመለክተው ነበር፤ ከዚህም በኋላ ያቺ መጋረጃ ወደ ሰማይ ተመለሰች፡፡

ጴጥሮስም ስላየው ራዕይ አደነቀ፤ ይህም ራዕይ ወደ ፈጣሪያቸው እግዚአብሔር የሚመለሱ አሕዛብን ስለመቀበል እንደሆነ አስተዋለ፤ ለወንሞቹ ሐዋርያትም አሕዛብ የእግዚአብሔርን ቃል እንደተቀበሉ የመቶ አለቃ ቆርኔሌዎስንም ከወገኖቹ ጋር እንዳጠመቀው ነገራቸው፡፡

ከዚህ በኋላም ጴጥሮስ ከዮሐንስ ጋራ ጌታችን እንዳዘዛቸው ወደ አንጾኪያ ከተማ ገቡ፡፡ የአገሪቱንም ሁኔታ ይጠይቅ ዘንድ ጴጥሮስ ዮሐንስን ላከው ሰዎችንም አግኝቶ ክፉ ነገር ተናገሩት፡፡ ሊገድሉትም ፈለጉ፤ እያለቀሰም ተመለሰ፤ ሰውነቱም ተበሳጨች ጴጥሮስንም አለው አባቴ ሆይ የእሊህ ጎስቋሎች ክፋታቸው እንዲህ ከሆነ ወደ ነገሥታቱና ወደ መኳንንቱ ገብተን በጌታችን ስም በሰበክን ጊዜ ምን እንሆን ይሆን እንዴትስ ሃይማኖትን እናስተምራለን፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስም ወዳጄ ሆይ የሃያውን ቀን መንገድ በአንዲት ሌሊት ያመጣን እርሱ ሥራችንን በአንዲት መልካም ያደርግልናልና አትፍራ፤ አትዘንም አለው፡፡ከዚህም በኋላ ወደ ከተማ መካከል ገብተው ክብር ይግባውና በጌታችን ስም ሰበኩ የከተማው ሰዎችና የጣዖታቱ አገልጋዮችም በእነርሱ ላይ ተሰበሰቡ ታላቅ ድብደባንም ደበደቧቸው፤ አጎሳቆሏቸውም፤ ግማሽ የራስ ጠጉራቸውንም ላጭተው ተዘባበቱባቸው፤ አሥውም በግንብ ውስጥ ጣሏቸው፡፡

ከዘህም በኋላ ተነሥተው ይረዳቸው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ጸለዩ፤ ወዲያውኑም ክብር ይግባውና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ኪሩቤልና ሱራፌል እያጀቡት ተገለጠላቸውና እንዲህ አላቸው፡፡ መረጥኋችሁ ጴጥሮስና ዮሐንስ ሆይ በዘመኑ ሁሉ እኔ ከእናነተ ጋራ እኖራለሁና አትፍሩ፤ አትዘኑም፡፡ ለመዘባበቻም በራሳችሁ መካከል ስለላጩአችሁ አታድንቁ ይህም መመኪያና ክብርን የክህነት ሥርዓትና ምልክትንም ይሆናችኋል፡፡ ካህን የሚሆን ሁሉ ያለዚህ ምልክት ሥጋዬንና ደሜን ማቀበል አይችልም፡፡

ይህ ምልክት እያለው የሚሞት ካህንም ኃጢአቱ ይሠረይለታል፡፡ ይህን ካላቸው በኋላ ከእርሳቸው ዘንድ በክብር ዐረገ፡፡ ከዚህም በኋላ ጳውሎስ መጥቶ ዮሃንስን ተገናኘው የዚህ አገር ሰዎች ያደረጉብህ ምንድነው እርሱም ስለ እኔ አታድንቅ የሐዋርያትንም አለቃ በእኔ ላይ ባደረጉት አምሳል አድርገውበታልና አለው፡፡ ጳውሎስም አጽናናቸው እንዲህም አላቸው እኔ በጌታችን ፈቃድ ወደ ከተማ ውስጥ ገብቼ እናንተንም አስገባችኋለሁ፡፡

ከዚህም በኋላ ጳውሎስ ሔዶ ምክንያትን ፈጠረ ጣዖታቸውንም እንደሚያመልክ መስሎ ሐዋርያትን እንዲያቀርቡለትና ስለ ሥራቸውም እንዲጠይቃቸው የከተማውን መኳንንት አነጋገራቸው፡፡መኳንንቱም ወደ ጳውሎስ እንዲያቀርቧቸው አዘዙ፤ በቀረቡም ጊዜ ጳውሎስ ስለ ሥራቸው ጠየቃቸው፡፡ እነርሱም ድንቆችንና ተአምራቶችን ለሚያደርግ ለክርስቶስ ደቀ መዝሙሮቹ እንደሆኑ ነገሩት፡፡ ዳግመኛም እናንተ እንደርሱ ማድረግ ትችላላችሁን አላቸው፡፡ እነርሱም አዎ በእርሱ ስም ሁሉን ሥራ መሥራት እንችላለን አሉት፡፡

ከዚህም በኋላ ከእናቱ ማሕፀን ዕውር ሆኖ የተወለደውን ዐይኑን አበሩ፡፡ የንጉሡንም ልጅ ከሞተ በሦስት ወሩ ሥጋውም ከተበላሸ በኃላ ከመቃብር አስነሡት፡፡ ንጉሡና የከተማ ሰዎች ሁሉ ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ፡፡ ጴጥሮስም ምድሩን ረግጦ ውኃን አፈለቀ፤ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም አጠመቋቸው በቀናች ሃማኖትም እንዲጸኑ አደረጓቸው፡፡

ከዚህም በኋላ በሎዶቅያ ያሉ ምእመናን የቂሳሮስ ባሕር ከወሰኑ አልፎ ብዙ ሰዎችን ከአትክልት ቦታዎቻቸውና ከከብቶቻቸው ጋራ እንዳሰጠማቸው ወደ ቅዱስ ጴጥሮስ ላኩ፤ ጴጥሮስም ተወዳጅ ዮሐንስን ወደ እነርሱ ላከ፡፡ዮሐንስም ወደ እነርሱ ሲጓዝ ዳና በግ አገኘ፤ በጉንም እንዲህ ብሎ ላከው፤ ወደ ቂሳሮስም ወንዝ ሒድ የክርስቶስ ደቀ መዝሙሩ ወደ አንተ ልኮናል ወደ ቀድሞው ወሰንህ ትገባ ዘንድ አንተ በእግዚአብሔር ቃል የታሰርክ ነህ ብሎሃል በለው፡፡ ያን ጊዜ በጉ እንዳዘዘው አደረገ፤ ወንዙም ሸሽቶ ወደ ቦታው ተመለሰ፡፡ ቁጥር የሌላቸው ብዙዎች የከተማ ሰዎችም ይህን አይተው በጌታ አመኑ፡፡

ከዚህም በኋላ ቅዱስ ጴጥሮስ አልፎ ወደ ሮሜ ከተማ ገባ በዚህም ሥፍራ መሠሪው ሲሞን ተቃወመው፤ እርሱንም ከአየር ላይ አውርዶ ጥሎ አጠፋው፤ ይህንንም ድንቅ ሥራ አይተው ብዙዎች ሕዝቦች አመኑ፡፡ የከተማው ገዥ የአክሪጶስ ቁባቶችም የጴጥሮስን ትምህርት ተቀበሉ፡፡ ሌሎችም የከበሩ ብዙዎች ሴቶች ትምህርቱን በመቀበል ከባሎቻቸው ርቀው ንጽሕናቸውን ጠበቁ፡፡

ስለዚህም ነገር ቅዱስ ጴጥሮስን ሊገድሉት የሮሜ መኳንንት ተማከሩ፡፡ የአልታብዮስ ሚስትም እንዳይገድሉት ከሮሜ ከተማ ወጥቶ እንዲሔድ ወደ ቅዱስ ጴጥሮስ ላከች፤ ምእመናን ወንድሞችም ውጣ አሉት፤ እርሱም ቃላቸውን ተቀበለ፡፡ ትጥቁንም ለውጦ ከከተማው ወጣ፡፡ በሚወጣበትም ጊዜ መስቀል ተሸክሞ ወደ ከተማ ሲገባ ጌታችንን አገኘውና አቤቱ ጌታዬ ወዴት ትሔዳለህ አለው፡፡ ጌታም ልሰቀል ወደ ሮሜ ከተማ እሔዳለሁ ብሎ መለሰለት፤ ቅዱስ ጴጥሮስም አቤቱ ዳግመኛ ትሰቀላለህን አለው፡፡

ያን ጊዜም ጎልማሳ ሳለህ ወገብህን በገዛ እጅህ ታጥቀህ ወደ ወደድከው ትሔዳለህ በሸመገልክ ጊዜ ግን እጅህን ታነሣና ሌላ ያስታጥቅሃል፤ ወደማትወደውም ይወስድሃል ያለውን የጌታችንን ቃል አሰበ አስተዋለውም፡፡ያን ጊዜም ወደ ከተማው ተመልሶ ክብር ይግባውና ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ የሆነውን ለወንድሞች ነገራቸው እነርሱም እጅግ አዘኑ፡፡

ንጉስ ኔሮን ቅዱስ ጴጥሮስን እንዲሰቅሉት አዘዘ፡፡ ሊሰቅሉትም በያዙት ጊዜ ወታደሮችን እንዲህ ብሎ ለመናቸው፡፤ የክብር ንጉስ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ላይ ሆኖ ስለተሰቀለ እኔ ቁልቁል ልሰቀል ይገባኛል፡፡ ወዲያውም እንደነገራቸው ሰቀሉት፡፡ ተሰቅሎ ሳለም ለምእመናን የሕይወትን ቃል አስተማራቸው በቀናች ሃማኖትም እንዲጸኑ አዘዛቸው ከዚህም በኋላ ነፍሱን በእግዚአብሔር እጅ ሰጠ፡፡

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በአባታችን በቅዱስ ጴጥሮስ ጸሎት ይማረን፤ በረከቱም ከእኛ ጋራ ይኑር ለዘላለሙ አሜን፡፡ ሰላም ለጳውሎስ ሃይማኖተ ክርስቶስ ዘአግሀደ፡፡ እስከ አቁሰልዎ በሰይፍ ወመተርዎ ክሣደ፡ ከመ ያግብእ ሕዝበ ሕየንተ ቀዳሚ ሰደደ፡፡ በላዕለ አብዳን ተመሰለ አብደ፡፡ ወለአይሁድኒ ኮኖሙ አይሁድ፡፡

በዚህችም ቀን ዳግመኛ ልሳነ ዕረፍት የክርስቶስ አንደበት የእውቀት አዘቅት የቤተ ክርስቲያን መብራት የቅዱስ ሐዋርያው ጳውሎስ የሰማዕትነቱ መታሰቢያ ነው፡፡ እንደ ስሙም ትርጓሜ መሪ አመስጋኝ ወደብ ጸጥታ ነው፡፡ይህም ጳውሎስ አስቀድሞ በክርስቶስ ያመኑትን የሚያሳድድ ነበረ፡፡ እርሱም ከብንያም ወገን የፈሪሳዊ ልጅ ነው፡፡ ወላጆቹም ሳውል ብለው ስም አወጡለት፤ ትርጓሜውም ስጦታ ማለት ነው፡፡ ቁመቱ ቀጥ ያለ፤ መልኩ ያማረ፤ ፊቱ ብሩህ፤ ቅላቱ እንደ ሮማን ቅርፍት ደበብ ያለ፤ ዐይኑም የተኳለ የሚመስል አፍንጫው ቀጥ ያለ ሸንጎበታም፤ ጉንጩ እንደ ጽጌረዳ ነበረ፡፡

እርሱም ሕገ ኦሪትን አዋቂ ነበረ፡፡ ለሕጉም ቀናተኛ ሆኖ ምእመናን አሳዳጅ ነበረ፡፡ ወደ ሊቀ ካህናቱም ሔዶ በመንገድ የሚያገኘው ሰው ቢኖር ወንዶችንና ሴቶችን እንደታሠሩ ወደ ኢየሩሳሌም ይመልሳቸው ዘንድ ለደማስቆ ከተማና ለምኩራቦች የፈቃድ ደብዳቤ ለመነ፡፡

ሲሔድም ወደ ደማስቆ ከተማ አቅራቢያ በደረሰ ጊዜ ድንገት ከሰማይ መብረቅ ድንገት ብልጭ አለበት፤ በምድር ላይም ወደቀ፤ ወዲያውም ሳውል ሳውል ለምን ታሳድደኛለህ የሚለውን ቃል ሰማ፡፡ ሳውልም አቤቱ አንተ ማነህ አለው፤ አንተ የምታሳድደኝ የናዝሬቱ ኢየሱስ ነኝ፤ በሾለው ብረት ላይ ብትረግጥ አንተን ይጎዳሃል አለው፡፡

እየተንቀጠቀጠም አደነቀ፤ አቤቱ ምን እንዳደርግ ትሻለህ አለው፡፡ ጌታም ተነሥና ወደ ከተማ ግባ ልታደርግ የሚገባህን ከዚያ ይነግሩሃል አለው፡፡ ከእርሱ ጋር ቆመው የነበሩ ሰዎችም ንግገሩን ይሰሙ ነበር፤ ነገር ግን የሚያዩት አልነበረም፡፡ ሳውልም ከምድር ተነሣ ዓይኖቹም ተገልጠው ሳሉ አያይም ነበር፤ እየመሩም ወደ ደማስቆ አስገቡት፡፡ በዚያም ሳያይ ሳይበላና ሳይጠጣ ሦስት ቀን ሰነበተ፡፡

በዚያም በደማስቆ ከደቀ መዛሙርት ወገን ሐናንያ የሚባል አንድ ሰው ነበረ፤ ጌታም በራእይ ተገለጠለትና ሐናንያ ብሎ ጠራው፡፡ እርሱም ጌታዬ እነሆኝ አለ፡፡ ተነሥና ቀጥተኛ ወደምትባለው መንገድ ሒድ በይሁዳ ቤትም ጠርሴስ ከሚባል አገር የመጣ ሳውል የሚባል ሰው ፈልግ፤ እርሱ አሁን ይጸልያልና አለው፡፡

ሐናንያ ግን መልሶ እንዲህ አለ፤ አቤቱ ስለዚህ ሰው በኢየሩሳሌም በቅዱሳኖችህ ላይ የሚያደርገውን ክፉ ነገር ሁሉ ከብዙ ሰዎች ሰምቻለሁ፤ ወደዚህም ከካህናቱ አለቃ አስፈቅዶ የመጣ ስምህን የሚጠሩትን ሁሉ ሊያስር ነው፡፡ ጌታችንም ተነሥና ሒድ በአሕዛብና በነገሥታት በእስራኤልም ልጆች ፊት ስሜን ይሸከም ዘንድ ለእኔ የተመረጠ ዕቃ አድርጌዋለሁና እኔም ስለ ስሜ መከራ ይቀበል ዘንድ እንዳለው አሳየዋለሁ፡፡

ያን ጊዜም ሐናንያ ሔደ፤ ወደ ቤትም ገባ፡፡ ወንድሜ ሳውል በመንገድ ስትመጣ የታየህ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታ ዘንድ የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ ይሞላብህ ዘንድ ወዳነተ ልኮኛል አለው፡፡ ያን ጊዜም የሸረሪት ድር የመሰለ ከዐይኖቹ ላይ ተገፎ ወደቀ፡፡ዐይኖቹም ተገለጡ፡፡ ወዲያውም አየ ተነሥቶም ተጠመቀ፡፡ እህልም በልቶ በረታ፡፡ ከደቀ መዛሙርትም ጋር በደማስቆ ለጥቂት ቀን ሰነበተ፡፡ በዚያው ጊዜ የእግዚአብሔር ልጅ ነው ብሎ ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ሰበከ፤ አስተማረም፡፡

የሰሙትም ሁሉ አደነቁ እንዲህም አሉ፤ በኢየሩሳሌም ይህን ስም የሚጠሩትን ያሳድድ የነበረ ይህ አልነበረምን ወደዚህስ የመጣው እያሠረ ወደ ሊቀ ካህናቱ ሊወስዳቸው አይደለምን፡፡ አጽናኝ መንፈስ ቅዱሰም አደረበት ዕውነተኛውንም ሃይማኖት ግልጽ አድርጎ አስተማረ፡፡

ለኦሪት ሕግ የሚቀና እንደነበረ እንዲሁ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሠራት ሕገ ወንጌል ዕጽፍ ድርብ ቅንዓትን የሚቀና ሆነ፡፡ ከዚህም በኋላ በአገሮች ሁሉ እየዞረ ሰበከ፤ በጌታችንም ስም ሰበከ፡፡ ድንቆችንና ተአምራትንም አደረገ፡፡ ቁጥር የሌላቸው አሕዛብንም አሳመናቸው ነገር ግን ብዙ ጊዜ በመገረፍ በመደብደብና በመታሠር ብዙ መከራ ደረሰበት፤ መከራውንም ሁሉ ታግሶ በሁሉ ቦታ ዞሮ አስተማረ፡፡

በሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ እንደተጻፈ የእግዚአብሔርን ሥራ ሲሠሩ ሲጾሙና ሲጸልዩ መንፈስ ቅዱስ እኔ እነርሱን ለመረጥሁለት ሥራ ሳውልንና በርናባስን ለዩልኝ አላቸው፡፡ ከዚህም በኋላ ጾመውና ጸልየው እጃቸውንም በራሳቸው ላይ ጭነው ሾሙአቸው፤ ከመንፈስ ቅዱስም ተሹመው ወደ ሴሌውቅያ ወረዱ፡፡

በደሴቱም ሁሉ ሲዘዋወሩ ጳፉ ወደምትባል አገር ደረሱ፡፡ በዚያም ሐሰተኛ ነቢይ የሆነ ስሙ በርያሱስ የሚባል አንድ ሥራየኛ አይሁዳዊ ሰው አገኙ፤ እርሱም ሰርግዮስ ጳውሎስ ከሚባል ብልህ ሰው ከሆነ አገረ ገዥ ዘንድ የነበረ ነው፡፡ የእግዚአብሔር ቃል ሊሰማ ወዶ በርናባስንና ሳውልን ጠራቸው፡፡ የስሙ ትርጓሜ እንዲህ ነበርና ኤልማስ የሚሉት ያ ሥራየኛ ሰው ይከራከራቸው ነበረ፤ ገዥውንም ማመን ሊከለክለው ወዶ ነበረ፡፡

ጳውሎስ በተባለው ሳውል ላይም መንፈስ ቅዱስ መላበት፡፡ አተኩሮም ተመለከተው፤ ኃጢአትንና ክፋትን ሁሉ የተመላህ የሰይጣን ልጅ የጽድቅ ሁሉ ጠላት ሆይ የቀናውን የእግዚአብሔርን መንገድ እያጣመምህ ተው ብትባል እምቢ አልህ እነሆ አሁን የእግዚአብሔር እጅ በአንተ ላይ ተቃጥታለች፤ ትታወራለህ እስከ ዕድሜ ልክህም ፀሐይን አታይም አለው፡፡ ወዲያውኑም ታወረ ጨለማም ዋጠው የሚመራውንም ፈለገ፤ አገረ ገዢውም የሆነውን አይቶ ደነገጠ በጌታችንም አመነ፡፡

ከዚህ በኋላ ሒደው ወደ ሊቃኦንያ ከዚያም ወደ ልስጥራንና ደርቤን ከተማ ወደ አውራጃውም ሁሉ ገብተው አስተማሩ፡፡ በልስጥራን ከተማም ከእናቱ ማሕፀን ጀምሮ እግሩ ልምሾ የሆነ አንድ ሰው ነበረ ተቀምጦ ይኖር ነበር እንጂ ልምሾ ከሆነ ጀምሮ ቆሞ አልሔደም፡፡ ጳውሎስንም ሲያስተምር ተመልከቶ ሃይማኖት እንዳለው እንደሚድንም ተረዳ፡፡ ድምጹንም ከፍ አድርጎ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተነሥና ቀጥ ብለህ ቁም እልሃለሁ አለው፤ ወዲያውኑ ተነሥቶ ሔደ፡፡

አሕዛብም ጳውሎስ ያደረገውን አይተው በጌታችን አመኑ፡፡ እርሱም በዚያ ሳለ አይሁድ ከአንጾኪያና ከኢቆንያ መጥተው ልባቸውን እንዲያስጨክኑባቸው አሕዛብንም አባበሉአቸው፡፡ ጳውሎስንም በደንጊያ ደበደቡት፤ ጎትተው ወደ ውጭ አወጡት፡፡በማግስቱም ከበርናባስ ጋራ ደርቤን ከተማ ሔዱ፡፡ በዚያችም ከተማ አስተማሩ ብዙ አሕዛብንም ሃይማኖት አስገቡ ለቤተ ክርስቲያንም ቀሳውስትን ሾሙላቸው፤ ከዚያም ወደ መቄዶንያ አልፈው ሔዱ ጋኔን ሟርት የሚያሥራትን አንዲት ልጅ አገኙ ከምታገኘው ዋጋ ለጌቶቿ ብዙ ትርፍን ታስገባ ነበር፡፡ እነዚህ ሰዎች የልዑል እግዚአብሔር አገልጋዮች ናቸው የሕይወትንም መንገድ ያስተምሯችኋል ብላ እየጮኸች ከጳውሎስ ኋላ ተከተለች፤ ብዙ ቀንም እንዲሁ ታደርግ ነበር፡፡ ጳውሎስንም አሳዘነችው መለስ ብሎም መንፈሰ ርኩስን በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም እንድትወጣ አዝዤሃለሁ አለው ወዲያውኑም ተዋት፡፡

ከዚህ በኋላም ሐለብ ከሚባል አገር ደረሰ፤ የጢሞቴዎስንም እናት ስሟ በድሮናን ከሞት አስነሣት፡፡ በዚያም ያዙት ለዚያች አገር ጣኦትም ሊሠዉት ወድደው በሚነድ እሳት ውስጥ ጨመሩት፡፡ ስለ እነርሱም እየማለደ እጆቹን በመስቀል ምልክት አምሳል ዘረጋ፡፡ አሕዛብም በአዩት ጊዜ ስለዚህ ድንቅ ሥራ አደነቁ፤ ከእሳት መካከልም እንዲወጣ ማለዱት፤ ምንም ምን ሳይነካው ወጣ ሰገዱለትም ክብር ይግባውና በጌታችንም አመኑ የአገሩ ሹም አርስጦስም አመነ፡፡

ሰባቱ የጣዖት ካህናት ግን ሸሽተው ተሠወሩ፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም በጭላት አምሳል የተቀረጸውን ምስል ጠራው ምስሉም በአንባሳ አምሳል መጥቶ በምኩራቡ መካከል በጳውሎስ ፊት ቆመ፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም የሚያመልኩህ ካህናቶችህ ወዴት አሉ አለው፤ አንበሳውም ያሉበትን አስክነግርህ ድረስ ጌታዬ ጥቂት ታገሠኝ፤ አለው፡፡ ካህናቱም ወደተሸሸጉበት ሔዶ አንዱን አንገቱን በአፉ ይዞ እየጎተተ አምጥቶ እንደ በድን በአደባባዩ መካከል ጣለው፡፡ ሰባቱንም እንዲሁ እያንዳንዱን እየጎተተ አመጣቸው፡፡

ሕዝቡም ሊገድሏቸው ወደዱ፡፡ ጳውሎስም ዛሬ በዚህች ከተማ ማዳን እንጂ መግደል አይገባም አለ፤ ከዚህም በኋላ ሁሉንም አጠመቃቸው፤ ሃይማኖትንም አስተማራቸው፡፡ ያንንም አንበሳ የሆነ የጭላት ምስል አንበሳ ሆይ አትፍራ ስለ አገለገልከኝ እሰከምሻህ ድረስ ኑሮህ በበረሀ ይሁን አለው ያን ጊዜም ወደ በረሀ ሔደ፡፡

ጳውሎስም ከዚያ ተነስቶ አካ ወደሚባል ከተማ ሔደ፡፡ ስክንትስ ከሚባል ደቀ መዝሙርም ጋር ተገናኘ፤ አይሁድም ዜናውን ሰምተው ከአሕዛብ ጋራ ተሰበሰቡ ይዘውም ጭንቅ የሆነ ስቃይን አሰቃዩት፤ ዳግመኛም ሁለት በሮችን አመጡ ከስክንጥስ ጋራም አሥረው በከተማው ጥጋጥግ በስለታም ድንጋይ ላይ አስጎተቷቸው ደማቸውም እንደ ውኃ ፈሰሰ፤ አጥንታቸውም እሰከሚታይ ድረስ ሥጋቸውም ተቆራረጠ፡፡ ወደ ጌታም ጸለዩ፤ ያን ጊዜም በሮቹ ከሚነዳቸው ጋራ ደንጊያ ሆኑ፡፡

ሕዝቡም በአዩ ጊዜ ለመኮንኑ ነገሩት እርሱም ተቆጣ ወደ እርሱም እንዲያቀርቧቸውና በደንጊያ እንዲወግሯቸው አዘዘ፤ በቅዱስ ጻውሎስም ላይ እጅግ ተቆጥቶ አንተ የሥራይ ሰው እነሆ አሠቃይሃለሁ አለው፡፡ በበሬ ቅርጽ የተሠሩ ሁለት ቀፎዎችንም ያመጡ ዘንድ አዘዘ፡፡ ዝፍት ሙጫና ድኝ አምጥተው በውጭ ቀላለቅለው ሁለቱን የናስ ቀፎዎች በውስጥም በውጭም ቀቧቸው፡፡ ሐዋርያትንም በውስጥ ጨምረው በእሳት ምድጃ ውስጥ አስገቧቸው፤ ሦስት መዓልትና ሦስት ሌሊትም እሳት አነደዱባቸው፡፡

መድኃኒታን ኢየሱስ ክርስቶስም ከመላእክቶቹ ጋራ መጣ እሳቱንም ከዚያ ፈልሶ ወደ ከተማ ውሰጥ ገብቶ የከተማውን ሰዎች ሁሉ እንዲከባቸው አደረገው፤ በተጨነቁም ጊዜ ጮኹ፤ አለቀሱም፡፡ መዳንን ከፈለጋችሁ ፈጥናችሁ በአደባባዩ በአንድነት ተሰብሰቡ የሚል ቃል ከሰማይ ጠራቸው፡፡ ጳውሎስም ወደ በረሀ አሰናብቶት የነበረው አንበሳ መጣ፤ ጳውሎስ በስሙ በሚያስተምርበት ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ እመኑ እያለ ጮኸ፡ ከዚህም በኋላ ወደ እሳቱ ምድጃ ተመልሶ ጳውሎስንና ስክንጥስን ከእሳቱ ውስጥ ውጡ አላቸው፤ ያን ጊዜም የራሳቸው ጠጉር እንኳ ሳይቀነብር ወጡ፤ በላያቸውም ላይ የቃጠሎ ሽታ የለም፡፡

ይህንን ድንቅ ሥራ አይተው በጌታችን በናዝሬቱ ኢየሱስ ክርስቶስ እናምናለን እያሉ ጮኹ፤ ከዚህም በኋላ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጠመቃቸው ስክንጥስንም ቅስና ሾመላቸው፡፡ከዚህ በኋላም ከሐዋርያ ፊልጶስ ጋራ ወደ ሁለት አገሮች በአንድነት ሔዱ፤ በዚያም በጌታችን ስም ሰበኩ የአገሩ አለቆችም ያዙአቸው እጆቻቸውንና እግሮቻቸውንም አሠሩአቸው በአንገቶቻቸውም የብረት ሰንሰለቶችንም አስገቡ ራሳቸውንም የሚሸፍን የብረት ቆብን ሠሩላቸው ዳግመኛም በእጅና በመሐል እጅ ጣቶችም ምሳሌ ሠርተው በእጆቻቸውና በክንዶቻቸው እያንዳንዱን የብረት እጅ ጨመሩ፡፡ ከብረቶችም ጋር ቸነከሩአቸው፡፡

ሁለተኛም እስከ አንገት የሚደርስ በትከሻ አምሳል ሠሩ፤ በፊትና በኋላም ቸነከሩአቸው፡፡ ደግሞም መላ አካላቸው ምንም እንዳይታይ የሚሽፍን የብረት ሠሌዳ ሠሩ፡፡ ከወገቦቻቸውም ጋራ ቸነከሩት፤ ችንካሮችም ተረከዛቸውን ነድለው ወደ ጭኖቻቸው እስከሚደርሱና እሰከ አቆሰላቸው ድረስ የብረት ጫማ ሠርተው እግሮቻቸውን ቸነከሩ፡፡

ደግሞ በመሸፈኛ አምሳል የብረት ሰናፊል ሠሩ፤ ቀማሚዎችም መጡ አንድ መክሊት የሚመዝን እርሳስንም አመጡ ታላቅ የብረት ጋንንም ሰባት ልጥር የሰሊጥ ቅባትን አመጡ፡፡ ስቡንና አደሮ ማሩን የእሳቱንም ኃይል አብዝቶ የሚነደውን ቅመሙን ከሙጫውና ከድኙ ጋር ቀላቀሉ፤ ከዋርካና ከቁልቋል ከቅንጭብም ደም ሰባት ልጥር አንድ የወይን አረግንና ቅባት ያላቸውን ዕንጨቶች ሁሉ አመጡ፡፡ በጋን ውስጥ ያበሰሉትንና ያሟሙትንም ልዩ ልዩ ቅመማ ቅመም አምጥተው ከሥጋቸው ጋራ እሰከሚጣበቅ በቅዱሳን ሐዋርያት ሥጋ ላይ ባሉት ሠሌዳዎች ውስጥ ጨመሩት፡፡ ከእግራቸው አስከ ራሳቸውም ከፍ ከፍ እስከሚል ድረስ በእሳት ያቃጠሉትን ያንን እርሳስ ጨመሩ፡፡ ርዝመቱ ዐስራ አምስት ክንድ በሆነ ወፍራም የጥድ ምሰሶ ላይም አቆሟቸውና ከበታቻቸው ፍሬ በሌለው በወይን ሐረግና በተልባ እሳቱን አቀጣጥለው አነደዱ፡፡ የእሳቱ ነበልባልም ከሥጋቸው በላይ ከፍ ከፍ አለ ሐዋርያ ግን ወደ እግዚአብሔር ይጸልዩ ነበር፡፡

ከመኳንንቱም በአንዱ ልብ ርኅራኄን አሳደረና እንዲፈቷቸው አዝዞ ፈቷቸው፡፡ በፈቷቸውና ሠሌዳውን ከሥጋቸው ላይ ባስወገዱ ጊዜ ቆዳቸው ተገፈፈና ከብረቱ ሠሌዳዎች ጋራ ወጣ፡፡ ብዙ ደምም ከሥጋቸው ጋር ፈሰሰ፡፡ ሰይጣንም በከተማው ሰዎች ልብ አደረና ሐዋርያትን ወደ እሳት ውስጥ መለሱአቸው፤ ያን ጊዜ ጌታችን ወርዶ የእሳቱን ነበልባል አጠፋው፡፡ ዝናምን የተመላች ብርህት ደመናም መጥታ ቅዱሳን ሐዋርያትን ከበበቻቸው፤ በዚያችም አገር አንድ ጊዜ በደንጊያ በመውገር አንድ ጊዜም በፍላጻ በመንደፍ ብዙ ተሠቃዩ፡፡ ከዚህም በኋላ ሙታንን በአነሡ ጊዜ የከተማው ሰዎች ሁሉ አመኑ፤ አጠመቋቸውም፤ ቤተ ክርስቲያንንም ሠሩላቸው፤ ካህናትንም ሾሙላቸው በቀናች ሃይማኖትም እስቲጸኑ አስተማሩአቸው፡፡ ከዚያም ወጥተው ጌታችን ወዳዘዛቸው ወደ ሌላ አገር ሔዱ፡፡

ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለጳውሎስ ተገለጠለትና የመረጥኩህ ጳውሎስ ሆይ ሰላም ላንተ ይሁን፡፡ መታሰቢያህን የሚያደርገውን፤ በስምህ ቤተ ክርስቲያን የሚሠራውንና፤ በውስጧም የሚጸልየውን ስለትንና መባንም የሚሰጠውን በመታሰቢያህም ቀን ለድሆች የሚመጸውተውን ሁሉ ካንተ ጋራ በመንግሥተ ሰማያት አኖራቸዋለሁ አለው፡ በስምህ የታነጹትንም አብያተ ክርስቲያናት መላእክቶቼን እንዲጠብቋቸው አደርጋቸዋለሁ፤ ብዙ ቃል ኪዳንም ሰጠው፡፡ በመለኮታዊ አፉ አፉን ሳመውና ከእርሱ ዘንድ ወደሰማያት በክብር ዐረገ፡፡

ከዚህም በኋላ እልዋሪቆን ወደምትባል ታላቅ ሀገር እስከሚደርስ በብዙ አገሮች ውስጥ ተመላለሰ፡፡ በዚያም የብርሃን እናት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተገልጻለት አረጋጋቸው፤ ረዳቸውም፡፡ በመጋቢት 29 እንደጻፍነው የአገሩን ሰዎች እንዲያጠምቃቸውና እንዲያስተምራቸው አዘዘችው፡፡

ከዚህም በኋላ ወደ ሮሜ ከተማ ገብቶ በውስጧ ሰበከ፤ በስብከቱም ብዙ ሰዎች አምነው የክርስትና ጥምቀትን አጠመቃቸው፡፡ በመጻሕፍትነት ያታወቁ ዐሥራ አራት መልእክቶችን ጻፈ፤ የመጀመሪያ መልእክቱም ለሮሜ የተጻፈችው ናት፡፡ መልካም ሩጫውንም ከፈጸመ በኋላ ንጉሥ ኔሮን ይዞ ጽኑ ሥቃይን አሠቃየው፡፡ ራሱንም በሰይፍ እንድቆርጡት ለሰያፊ ሰጠው፤ ከሰያፊውም ጋራ አልፎ ሲሔድ ከንጉሥ ኔሮን ዘመዶች ወገን የሆች አንዲት ብላቴና አገኘቸው፤ እርሷም ክብር ይግባውና በጌታችን ያመነች ነበረች፤ ለእርሱም አለቀሰች፡፡ እርሱ ግን መጎናጸፊያሽን ስጪኝ እኔም ዛሬ እመልስልሻለሁ አላት፡፡ እርሷም መጎናጸፊያዋን ሰጠችውና ራስ ወደሚቆርጡበት ቦታ ሔደ፡፡ ለሰያፊውም ራሱን ባዘነበለ ጊዜ በመጎናጸፊያዋ ፊቱን ሸፈነ፤ ሰያፊውም የቅዱስ ጳውሎስን ራስ ቆርጦ በዚያች ብላቴና መጎናጸፊያ እንደተሸፈነ ጣለው፡፡

ሰያፊውም ጳውሎስን እንደገደለው ለንጉሥ ሊነግረው በተመለሰ ጊዜ ያቺ ብላቴና አገኘቸው፤ ያ ጳውሎስ ወዴት አለ አለችው ራስ በሚቆረጥበት ቦታ ወድቋል ራሱም በመጎናጸፊያሽ ተሸፍኗል አላት፡፡ እርሷም እንዲህ ብላ መለሰችለት፤ ዋሽተሃል እነሆ ጴጥሮስና ጳውሎስ በእኔ ዘንድ አልፈው ሔዱ እነርሱም የመንግሥት ልብሶችን ለብሰዋል፤ በራሳቸውም ላይ በዕንቁ የተጌጡ ዐይንን የሚበዘብዙ አክሊላትን አድርገዋል፡፡ መጎናጸፊያዬንም ሰጡኝ፤ አርሷም እነኋት ተመልከታት ብላ ለዚያ ሰያፊ አሳየችው ከእርሱ ጋራ ለነበሩትም አሳየቻቸው፡፡ አይተውም አደነቁ፤ ስለዚህም ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ፡፡የዚህም ሐዋርያ ጳውሎስ ተአምራቶቹ ቁጥር የሌላቸው እጅግ የበዙ ናቸው፡፡

ለእግዚአብሔር ምሥጋና ይሁን እኛንም በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት፤ ከሁሉም ሊቃነ ጳጳሳት፤ እና የቅድስት የሐዋርያት ቤተ ክርስቲያን ልጆች ጋር ይኑር ለዘላለሙ አሜን፡፡

  • ምንጭ፡- መጽሐፈ ስንክሳር ዘወርኀ ሐምሌ

 

 

የማቴዎስ ወንጌል

 ሐምሌ 3 ቀን 2006 ዓ.ም.

ምዕራፍ አራት

በዚህ ምዕራፍ መጀመሪያ ያለው ንባብ የሚተርክልን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከተጠመቀ በኋላ ሳይውል ሳያድር በኢያሪኮ አካባቢ ወደሚገኘው /ሣራንደርዮን/ የአርባ ቀን ተራራ ተብሎ ወደሚታወቀው ሥፍራ ወጣ፡፡ በዚያም ዐርባ መዓልትና ዐርባ ሌሊት ጾመ፣ ከዚህ በኋላ ተራበ፤ ጸላኤ ሠናይት ዲያብሎስ ሦስት ፈተናዎችን አቀረበለት፡፡

የመጀመሪያው ፈተና መራቡን አይቶ ድንጋይ በማቅረብ እነዚህን ባርከህ ወደ ዳቦነት ለውጥ አለው፡፡ ጌታችንም የሰይጣን ታዛዥ በመሆን የሚገኘውን ሲሳይ በመንቀፍ “ሰው በእግዚአብሔር ቃል እንጂ በእንጀራ ብቻ አይኖርም” አለው፡፡ በሦስት ሲፈትነው በትዕግሥት አሸነፈው፡፡

ዳግመኛው በትዕቢት ይፈትነው ዘንድ አሰበ፡፡ ጌታም ሐሳቡን ዐውቆ ወደ መቅደስ ጫፍ ሄደለት፡፡ ፈታኙም ከቤተ መቅደስ ጫፍ ዘሎ እንዲወርድ የመጽሐፍ ቅዱስን ጥቅስ ጠቅሶ ጠየቀው፡፡ ጌታም “ጌታ አምላክህን አትፈታተነው ተብሎ ተጽፎብሃል” ብሎ ጠቅሶ መዞ የመጣውን ሰይጣን ጥቅስ ጠቅሶ አፉን አስያዘው መዝ.90፡11፤ ዘዳ.6፡16፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለሚጠይቋችሁ ሁሉ መልስ ለመስጠት የተዘጋጃችሁ ሁኑ ማለቱ ይህንን ይዞ ነው፡፡ 1ኛ ጴጥ.3፡15፡፡

ፈታኝ ዲያብሎስም የቀደሙት ሁለቱ ፈተናዎቹ ጌታን እንዳልጣሉት ባየ ጊዜ ሦስተኛ ፈተናውን አቀረበ፡፡ የዓለምን ግዛት ከነክብሩ አሳየውና “ወድቀህ ብትሰግድልኝ ይህን ሁሉ እሰጥሃለሁ” አለው፡፡ ጌታም “ሂድ አንተ ሰይጣን ለጌታህ ለአምላክህ ስገድ እርሱንም ብቻ አምለክ ተብሏል” ብሎ በመመለስ በፍቅረ ንዋይ ያቀረበለትን ፈተና ገንዘብን በመጥላት አሸንፎታል፡፡

እነዚህም ጌታ የተፈተነባቸው ሦስቱ ፈተናዎች ዛሬ ሰው የሚፈተንባቸው ዋና ዋና ኃጢአቶች ናቸው፡፡ እርሱም እነዚህን መርጦ የተፈተነበት ለአርአያ ነው፡፡ ድል ማድረግ የምንችልበትን መንገድም አብነት ሆኖ አሳይቶናል፡፡ ከዚህ በኋላ የማስተማር ሥራውን በተለያዩ ቦታዎች ጀመረ፡፡ ደቀ መዛሙርቱንም ከየቦታው ጠራ፡፡

 

  • ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 4ኛ ዓመት ቁጥር 1 መስከረም 1989 ዓ.ም.

 

a tenat 2006 1

የንባብ ባህልን ለማሳደግ ቤተ ክርስቲያን የሚኖራት ድርሻ ከፍተኛ መሆኑ ተገለጸ

 ሐምሌ 1 ቀን 2006 ዓ.ም.

ይብረሁ ይጥና

a tenat 2006 1ከፍተኛ ድር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ትርጉም ያለው የንባብ ባሕልን ለማሳደግ ከፍተኛውን ድርሻ መያዝ እንደሚገባት በማኅበረ ቅዱሳን የጥናትና ምርምር ማእከል ባዘጋጀው የንባብ ባሕል አስመልክቶ በቀረበ የጥናት ጉባኤ ላይ ተገለጸ፡፡

ሠኔ 28 ቀን 2006 ዓ.ም. ለግማሽ ቀን በማኅበሩ ሕንፃ ላይ በተካሔደው ጉባኤ ትርጉም ያለው የንባብ ባሕል በዕውቀት እና በሥነ ምግባር የታነፀ ዜጋ ለማፍራት በሚል መሪ ቃል የተዘጋጀ ሲሆን፤ “የንባብ ባሕልን ለማሳደግ የተለያዩ አካላት ሚና” ፤ እንዲሁም “ትርጉም ያለው የንባብ ባሕል በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን” በሚሉ ሁለት ርእሰ ጉዳች ላይ የተደረጉ ጥናቶች ቀርበዋል፡፡

በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የአማርኛ ቋንቋ፤ ሥነ ጽሑፍና ፎክሎር መምህር የሆኑት መምህር ደረጀ ገብሬ “የንባብ ባህል ለማሳደግ የተለያዩ አካላት ሚና” በሚል ርእስ ባቀረቡት ጥናት፤ የንባብ ምንነት፤ የንባብ ክሂል የእድገት ደረጃዎች፤ የማንበብ ጠቃሚነት፤ የማንበብ ባሕልን የማሳደግና የማዳበሪያ ሥልቶቹ ምን እንደሆኑ በስፋት ዳስሰዋል፡፡ በተለይም ሕፃናት የቋንቋ ችሎታቸውን በማዳበር በየጊዜው የማዳመጥና የማንበብ ፍላጎታቸውን ማሳደግ እንደሚቻል ገልጠዋል፡፡

ለንባብ ባሕል መዳበር ትምህርት ቤቶችና ወላጆች፤ መንግሥትና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ትኩረት ሠጥተው መሥራት እንደሚገባቸውም በጥናታቸው አመልክተዋል፡፡ “ትርጉም ያለው የንባብ ባህል በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን” በሚል ርእስ ጥናታቸውን ያቀረቡት አቶ ጸጋዘአብ ለምለም ደግሞ ትርጉም ያለው የንባብ ባሕል ለፈጣሪነት፤ ለውጤታማነት፤ ለብቁ ተወዳደሪነትና ለሀገር ሁለንተናዊ ብልጽግና ጠቀሜታው የጎላ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

ዓለም አቀፋዊት የሆነችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የብዙ መጻሕፍትና መዛግብት እንዲሁም ቅርሶች ባለቤት እንደመሆኗ መጠን አገልግሎቷን ካለንባብ ማሰብ አስቸጋሪ እንደሚያደርገው አመልክተው፤ ቤተ ክርስቲያን በርካታ ምሥጢራት እንዳሏት ሁሉ እነዚህን ምሥጢራት ለአገልግሎት ለማብቃት ትርጉም ያለው የንባብ ባሕል አስፈላጊነትና ንባብ የቤተ ክርስቲያኗ አንዱ አካል መሆኑን በጥናታቸው ዳስሰዋል፡፡

ንባብ ሲባል ከፊደል ቆጠራ ጀምሮ ያለው ሲሆን፤ ቤተ ክርስቲያን የፊደል ባለቤት ሆና ብትቀጥልም ትርጉም ያለው የንባብ ባሕል አድማሷን አለማስፋፋቷን በስፋት አቅርበዋል፡፡ የዐቅም ማጣት ሳይሆን ዐቅምን አለማወቅ፤ የአጠቃቀም ችግር፤ ተቋማዊ የሆነ አስተዳደር አለመዘርጋት፤ ቤተ ክርስቲያን ከዘመኑ ቴክኖሎጂ ጋር አለመተሳሰሯ፤ ንባብን እንደ አንድ የአገልግሎት አካል አለመመልከት እንደ ምክንያትነት ተጠቅሰዋል፡፡

ቤተ ክርስቲያን ትርጉም ያለው የንባብ ባሕል አድማስን ለማስፋፋት ንባብን እንደ ሃይማኖታዊ በዓል አከባበራችን ባሕል ማድረግ፤ ዐቅምን ማሳደግና ማበልጸግ፤ ጠንካራ ተቋማዊ አስተዳደርን መዘርጋት፤ ከዘመኑ ቴክኖሎጂ ጋር ማስተሳሰር፤ የጥናትና ምርምር ማእከላትን ማበራከት የመሳሰሉትን ጥናት አቅራቢው እንደ መፍትሔ አቅርበዋል፡፡

በቀረቡት ሁለቱም ጥናታዊ ጽሑፎች ላይ ከተሳታፊዎች ጥያቄዎች ቀረበው በባለሙያዎቹ ማብራሪያ ተሰጥቶባቸዋል፡፡

 

a menfesawy 2006 1

የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ደቀመዛሙርትን አስመረቀ

 ሰኔ 30 ቀን 2006 ዓ.ም.

ዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ

a menfesawy 2006 1በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ በቀንና በማታ መርሐ ግብር ያስተማራቸውን ሦስት መቶ ደቀመዛሙርት አስመረቀ፡፡

ሰኔ 28 ቀን 2006 ዓ.ም. በጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ ተገኝተው ለተመራቂ ተማሪዎች የእንኳን ደስ ያላችሁ መልእክት ያስተላለፉት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት “የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን እምነቷን፤ ትውፊቷንና ታሪኳን እንደተጠበቀ ለትውልዱ ሁሉ እንድታደርሱላት አደራ ተረክባችኋል” ብለዋል፡፡

የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ጠባቂ ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ በበኩላቸው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ያሏትን ሦስት ኮሌጆች አቅም ለማሳደግ ከዚህ ቀደም የሰጠችውን ትኩረት በማጠናከር ውጤታማ ማድረግ ይኖርባታል ሲሉ ተናግረዋል፡፡

ከተመራቂ ደቀመዛሙርቱ መካከል ከዚህ በፊት ከነበረው በተሻለ ሁኔታ የሴት ተማሪዎች ቁጥር ከፍ ማለቱንና በማስተርስና በዲፕሎማ መርሐ ግብር ከፍተኛ ውጤት ማስመዝገብ መቻላቸው ተገልጧል፡፡

በዚህ ዓመት ኮሌጁ ካስመረቃቸው ደቀመዛሙርት መካከል 25 በማስተርስ፤ 71 በመጀመሪያ ዲግሪ፤ 114 በዲፕሎማ፤ 7 በግእዝ ዲፕሎማ፤ እንዲሁም 83 በርቀት ትምህርት በሰርተፊኬት ትምህርታቸውን ተከታትለው መመረቃቸውን ከኮሌጁ ሬጅስትራር ክፍል የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡

 

 

ge awd 2006 44

ዐውደ ርዕዩ ተጠናቀቀ

ሰኔ 30 ቀን 2006 ዓ.ም.

አውሮፓ ማእከል የጀርመን ቀጠና ማእከል

በሀገረ ጀርመን ፍራንክፈርት ከተማ ለሦስት ቀናት ለሕዝብ ክፍት ሆኖ የቆየው ዐውደ ርዕይ ተጠናቀቀ፡፡

ge awd 2006 44
“ለሁለንተናዊ የቤተ ክርስቲያን እድገት የድርሻችንን እንወጣ” በሚል ርዕስ ተዘጋጅቶ ሲታይ የሰነበተው ዐውደ ርእይ በፍራንክፈርትና አካባቢው በሚኖሩ በርካታ ምእመናን ተጎብኝቷል፡፡ ዐውደ ርእዩን የጎበኙ ምእመናንም ባዩት ነገር እንደተደሰቱና ብዙ ትምህርት እንዳገኙበት ገልጸዋል፡፡

ዝግጅቱ በልዩ ልዩ የጀርመንና የአውሮፓ ከተሞች ቢደረግ ምእመናን ስለ ቤተ ክርስቲያናቸውና እምነታቸው በቂ ግንዛቤ እንዲያገኙ ስለሚረዳቸው በተከታታይ እንዲቀርብ የዐውደ ርዕዩ ተሳታፊዎቹ ለኮሚቴው የአደራ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡ ከዐውደ ርዕዩ ጎን ለጎንም ሰፊ የስብከተ ወንጌልና የምክር አገልግሎት ከኢትዮጵያ በመጡ መምህራን ሲሰጥ ሰንብቷል፡፡

በአጠቃላይ ዐውደ ርዕዩ እንደታሰበው የተከናወነና ውጤታማ እንደነበር ዐውደ ርእዩን ያዘጋጀው በማኅበረ ቅዱሳን የጀርመን ቀጠና ማእከል አባላት ገልጸዋል፡፡

 

ge awd 2006 2

“ለሁለንተናዊ የቤተ ክርስቲያን እድገት የድርሻችንን እንወጣ” ዐውደ ርዕይ ተከፈተ

ሰኔ 28 ቀን 2006 ዓ.ም.

አውሮፓ ማእከል የጀርመን ቀጠና ማእከል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የማኅበረ ቅዱሳን የአውሮፓ ማእከል የጀርመን ቀጠና ማእከል በፍራንክፈርት ከተማ ኢኮነን ሙዚየም ያዘጋጀው ዐውደ ርእይ ተከፈተ፡፡ge awd 2006 2

 

ከሰኔ 27- 29 ቀን 2006 ዓ.ም./July 4-6, 2014/ እንዲታይ የተዘጋጀው ዐውደ ርእይ ጥሪ የተደረገላቸው ካህናትና ምእመናን በተገኙበት በልዩ ልዩ ዝግጅቶች ተከፍቷል፡፡ ጸሎተ ወንጌል በቦታው በተገኙ ካህናት ተደርጓል፤ የዐውደ ርእዩን የዝግጅት ሒደትና ይዘት አስመልክቶም አቶ ቃለ አብ ታደሰ የዝግጅት ኮሚቴው ሰብሳቢ የመክፈቻ ንግግር አድርገዋል፡፡

እንደ አቶ ቃለ አብ ገለጻ የጥንታዊቷንና የሐዋርያዊቷን ቤተ ክርስቲያን ታሪክ፣ ባሕልና ትውፊት ማስተዋወቅን ዓላማው ያደረገው ዝግጅቱ በሦስት ዋና ዋና ክፍሎች ተከፋፍሎ የተዘጋጀ ነው፡፡ የመጀመሪያው ክፍል የቤተ ክርስቲያኗን ታሪክ በአጭሩና ተመልካች በቀላሉ ሊረዳው በሚችለው መንገድ የቀረበበት የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ነው፡፡  ሁለተኛው ደግሞ የዕውቀትና የጽድቅ እንዲሁም የልማት መሠረቶች የነበሩት ገዳማትና አድባራት እንዲሁም አብነት ት/ቤቶች ያደረጉትን አስተዋጽዖና በአሁኑ ወቅት እያጋጠማቸው ያለው ተግዳሮቶች በዝርዝር የቀረቡበት ነው፡፡ የመጨረሻው ደግሞ ከግንቦት 1984 ዓ.ም ጀምሮ ሰፊ መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎቶችን ሲሰጥ የቆየውና ወደፊትም የሚሰጠው ማኅበረ ቅዱሳን ታሪክ፣ አገልግሎትና በየጊዜው ያጋጠሙት ችግሮች የቀረቡበት ክፍል ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን በአውሮፓ ያላት የአገልግሎት ታሪክ የተዳሰሰበት አንዱ የመርሐ ግብሩ አካል ነበር፡፡

 

ge awd 2006 1በክብር እንግድነት ተገኝተው ዐውደ ርዕዩን በጸሎት የከፈቱት መልዐከ ፀሐይ ቆሞስ አባ ሲራክ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምስራቅና ምዕራብ አውሮፓ ሀገረ ስብከት የፍራንክፈርት ደብረ ፀሐይ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ ናቸው፡፡ መልአከ ፀሐይ በመክፈቻ መርሐ ግብሩ ላይ የተከፈተው ዐውደ ርዕይ በፍራንክ ፈርት ከተማ ለአራተኛ ጊዜ እንደኾነ በማውሳት፤ ሁሉንም ዐውደ ርእዮች አዘጋጅቶ ለፍራንክፈርት ከተማና አካባቢው ሕዝብ ለዕይታ ያቀረበው በማኅበረ ቅዱሳን የጀርመን ቀጠና ማእከል ምስጋና ይገባዋል ብለዋል፡፡ ማኅበሩ ለቤተ ክርስቲያን እየሰጠ ያለው አገልግሎት ሰፊና ጠቃሚ ነው ያሉት መልአከ ፀሐይ ቆሞስ አባ ሲራክ፤ ለዚሁ ደግሞ እኔ ራሴ ምስክር ነኝ በማለት በቅርብ ጊዜ ወደ ኢትዮጵያ ሔደው ማኅበሩ በአቡነ  ቶማስ ዘደብረ ሃይዳ ገዳም እያደረገ ያለውን የልማት እንቅስቃሴ በአብነት ጠቅሰዋል፡፡

 

የዐውደ ርእዩን መከፈት አስመልክቶ አስተያየት እንዲሰጡ የተጠየቁት ምእመናንም በዝግጅቱ እንደተደሰቱ ገልጸዋል፡፡ በፍራንክፈርት ከተማ ነዋሪ የኾኑት አቶ ነቢዩ የማነ፤ ላለፉት ሦስት ጊዜያት የቀረቡትን ዝግጅቶች እንደተመለከቱ አውስተው «ይኸኛውም ዝግጅት ብዙ ያላወኳቸውን ነገሮች አሳውቆኛል፡፡ ይልቁንም የቤተ ክርስቲያኗ ልጆች ምን ያህል ሓላፊነታችንን እንዳልተወጣን አስገንዝቦኛል፤ ይህም በእውነት ቁጭት ፈጥሮብኛል፡፡  ማኅበረ ቅዱሳን በሀገር ቤትም ይሁን በውጭ የሚሰጠው አገልግሎት በእጅጉ እየጠቀመን ነውና ሁሉም ቢደግፈው» በማለት ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡

 

በተመሳሳይ ሁኔታም በከተማው ነዋሪ የኾኑት ወ/ሮ እጥፍ ወርቅ ወልዴ ባዩት ዝግጅት ብዙ ነገር እንዳወቁና «ሁሉም በውጭ የሚኖረው ምእመን በሀገራችን በችግር ላይ ያሉትን ገዳማትንና አድባራትን እንዲሁም አብነት ት/ቤቶችን ለዕረፍትም ይሁን ለልዩ ልዩ ጉዳዮች ወደ ሀገር ቤት ስንሔድ በአካል በመገኘት ልናያቸው ይገባል፤ አይተንም መርዳት ይጠበቅብናል፤» ብለዋል፡፡  አቶ ኤልያስ መሸሻ ደግሞ በስዊዘርላን ነዋሪ የኾኑና ዝግጅቱ ብቁ ቁም ነገሮችን እንዳሳወቃቸው ጠቅሰው፤ «ይህን መሰሉ ድንቅና ጠቃሚ ዝግጅት በሁሉም የአውሮፓ ከተሞች ተዘዋውሮ ሊታይ ይገባዋል» ብለዋል፡፡

 

እስከ እሑድ ሰኔ 29 ቀን 2006 ዓ.ም. /July 6, 2014/ ድረስ የሚቆየውና በበርካታ ምእመናንና ጀርመናውያን እንደሚጎበኝ የሚበሚጠበቀው በዚህ ዝግጅት ጥናታዊ ጽሑፎችና የቤተ ክርስቲያኗን ልዩ ልዩ ባሕሎች የሚያስተዋውቁ ትዕይንቶችና ስብከተ ወንጌል ይቀርባሉ፡፡

 

በሀገረ ጀርመን አስራ አንድ አብያተ ክርስቲያናት የሚገኙ ሲኾን ሁሉም በደቡብ ምስራቅና ምዕራብ አውሮፓ ሀገረ ስብከት ስር የታቀፉና አገልግሎት የሚሰጡ ናቸው፡፡ መንበረ ጵጵስናውን በፍራንክፈርት ከተማ ያደረገው ሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስም ብፁዕ አቡነ ሙሴ ናቸው፡፡        


a 27 2006 1 1

ከአጤ ዋሻ ተዘርፎ የነበረው ታቦተ መድኃኔዓለም ወደ መንበረ ክብሩ ተመለሰ

 ሰኔ 27 ቀን 2006 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

a 27 2006 1 1ከሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ደብረ ብርሃን ከተማ በአሥር ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ከሚገኘው የአጤ ዋሻ ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ተዘርፎ ጅቡቲ ውስጥ ለ17 ዓመታት ተደብቆ የነበረው ታቦተ መድኃኔዓለም ወደ አዲስ አበባ ተመልሶ ሰኔ 21 ቀን 2006 ዓ.ም. ወደ መንበረ ክብሩ ገብቷል፡፡ /ሚያዚያ 17 ቀን 2006 ዓ.ም. ታቦቱ ከጅቡቲ ወደ አዲስ አበባ መግባቱን ከዚህ በፊት መዘገባችን ይታወሳል/፡፡ 

ታቦቱ ሐምሌ 27 ቀን 1989 ዓ.ም. ሌሊት ማንነታቸው ባልታወቁ ግለሰቦች ተሰርቆ ለ17 ዓመታት ጅቡቲ ውስጥ በአንድ የሌላ እምነት ተከታይ ቤት ውስጥ ተደብቆ ከቆየ በኋላ ጅቡቲ ለሚገኘው ለምሥራቀ ፀሐይ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን አስተዳደሪ ለአባ ዮናስ መልከ ጼዲቅ ከቤተሰቡ መካከል በአንዱ መረጃው ይደርሳቸዋል፡፡ አባ ዮናስ በደረሳቸው መረጃ መሠረት ለጠቅላይ ቤተ ክህነት በማሳወቅ ታቦቱን ለማስመለስ ከፍተኛ ጥረት ተደርጓል፡፡

a 27 2006 1 2ሚያዚያ 17 ቀን 2006 ዓ.ም. ወደ አዲስ አበባ ተመልሶ በጠቅላይ ቤተ ክህነት የቅርስ ጥበቃና ቤተ መዘክር ለጊዜው እንዲቀመጥ በማድረግ፤ በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ሰኔ 21 ቀን 2006 ዓ.ም. በከፍተኛ መንፈሳዊ ሥነ ሥርዓት ወደ አጤ ዋሻ ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን አሸኛኘት ተደርጎለታል፡፡

የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ኤፍሬም፤ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ መዘምራንና ምእመናን በደብረ ብርሃን ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ለታቦቱ ደማቅ አቀባበል በማድረግ በአጤ ዋሻ ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ወደ መንበረ በክብሩ አስገብተውታል፡፡

ብፁዕነታቸው በሰጡት ቃለ ምእዳን ለታቦቱ መመለስ ከፍተኛ ጥረት ላደረጉ አካላት ምሥጋናቸውን አቅርበው ምእመናን በተለይም በየአጥቢያው የሚገኙ ወጣቶች ቤተ ክርስቲያንን እንዲጠብቁ የአደራ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

ወደ አጤ ዋሻ ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ለመድረስ በጣም አስቸጋሪና ውጣ ውረድ የተሞላበት ገደልን መውረድ ስለሚጠይቅ በርካታ የቤተ ክርስቲያን የከበሩ ንዋያተ ቅድሳት በኢጣሊያ ወረራ ወቅት ተሸሽገውበት እንደነበር የቤተ ክርስቲያኑ አገልጋይ አባቶች ይገልጻሉ፡፡ ከእነዚህም መካከል የኢጣሊያ ጦር በአድዋ ጦርነት ድል እንዲነሱ ካደረጋቸው አንዱ የመናገሻ ገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ታቦት በመሆኑ ይህንን ታቦት ለመዝረፍ ከ1928 ዓ.ም. ጀምሮ የኢጣሊያ ጦር ኢትዮጵያን በወረረበት ወቅት ከፍተኛ ጥረት አድርጓል፡፡ ነገር ግን ለሃይማኖታቸውና ለሀገራቸው ፍጹም ፍቅር የነበራቸው አባቶች ታቦቱን ከቤተ መቅደስ በማውጣት ጦርነቱ እስኪያበቃ አጤ ዋሻ ወስደው ሸሽገውታል፡፡

ከጦርነቱ ማብቃት በኋላ በ1937 ዓ.ም. ካህናቱ ታቦቱን አጅበው ከአጤ ዋሻ ወደ አዲስ አበባ መልሰውታል፡፡ ዐፄ ኃይለ ሥላሴ ካህናቱ በታማኝነት ታቦቱን ጠብቀው በማኖርና በክብር በመመለሳቸው በወርቅ የተለበጠ የመድኃኔዓለም ታቦት ይዘው እንዲመለሱ አድርገዋል፡፡

ከ1937 ዓ.ም. ጀምሮ አገልግሎት ሲሰጥ የነበረው ይህ ታቦት በ1989 ዓ.ም. ተሰርቆ ጅቡቲ ውስጥ በሌላ እምነት ተከታይ ቤት ውስጥ ተደብቆ ቆይቷል፡፡ በቤቱ ውስጥ ደብቆ ያስቀመጠው ግለሰብ የተሰደደ ሲሆን፤ ሚስቱ ስታብድ ልጁ ሞቶበታል፡፡ በዚህ የተደናገጠው ሌላው የሰውየው ልጅ በቤታቸው ውስጥ ታቦት እንዳለና ወደ ቤተ ክርስቲያን እንዲወሰድ ራሱ መጥቶ መረጃ በመሥጠቱ ታቦቱ ወደነበረበት በክብር ተመልሷል፡፡

 

ክረምት

ሰኔ 25 ቀን 2006 ዓ.ም.

መ/ር ሳሙኤል ተስፋዬ

በቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ በዕለተ ረቡዕ የተፈጠሩት ፀሐይ፣ ጨረቃና ከዋክብት ቀን ለመቁጠር፣ዘመንን፣ ወራትን፣ በዓላትንና አጽዋማትን ለማወቅ ወሳኝ ፍጥረቶች ናቸው፡፡ ዘፍ.14-19፣ ዘዳ.12፡1፡፡

እንደ ቤተ ክርስቲያናችን አቆጣጠር አንድ ዓመት በፀሐይ አቆጣጠር 365 1/4 ቀናት፡፡ በጨረቃ አቆጣጠር 354 ቀናት፡፡ በከዋክብት አቆጣጠር ጸደይ፣በጋ፣መጸውና ክረምት የተባሉ አራት ወቅቶች አሉ፡፡

ወቅት እንዲፈራረቅ በዘመን ላይ የተሾሙ ዓመቱን በአራት ክፍለ ዘመን የሚገዙት አራት ከዋክብት ሲሆኑ በእያንዳንዱ ወር ላይ የሰለጠኑ ከአራቱ ከዋክብት ሥር እንደ ወታደር የሚያገለግሉ ሦስት ሦስት ወታደሮች በድምሩ 12 ከዋክብት አሉ፡፡ እነዚህ ከዋክብት ወቅቶቹ ሥርዐታቸውን ጠብቀው እንዲሸጋገሩ የሚያደርጉና የእግዚአብሔር ጸጋ ለፍጥረቱ እንዲደርስ የሚያደርጉ ናቸው፡፡

ዓመቱን ለአራት ወቅቶች የሚከፈሉትና የሚመግቡት ከዋክብት የሚከተሉት ናቸው፡-

ምልክኤል፡-

በጸደይ የሰለጠነው ኮከብ ምልክኤል ሲሆን በሥሩ ያሉት ሦስት ከዋክብት/ወታደሮች/ ሚዛን በመስከረም ወጥቶ 30 ዕለት ከ 10 ኬክሮስ የሚታይ መልኩ እንደ ሚዛን ነው፡፡ አቅራብ በጥቅምት ወጥቶ 29 ዕለት ከ40 ኬክሮስ የሚታይ መልኩ እንደ ጊንጥ ነው ፡፡ ቀውስ በኅዳር ወጥቶ 29 ዕለት ከ28 ኬክሮስ የሚታይ መልኩ እንደ ቀስት ነው፡፡ (ኬኪሮስ ማለት ረጅም መስመር ማለት ሲሆን የቀንና የሌሊት ሰዓቶች ክፍል ነው፡፡ ከምሥራቅ እስከ ምዕራብ ተዘርግቶ 60 ክፍሎች አሉት፡፡ ፀሐይ ጨረቃ ከዋክብት ሁል ጊዜ እየሄዱበት በየቀኑ አንድ ጊዜ ያልፍበታል፡፡ 5 ኬክሮስ 1 ሰዓት ነው፡፡)

ናርኤል፡-

በበጋ የሰለጠነው ኮከብ ናርኤል ሲሆን በሥሩ ያሉት ሦስት ከዋክብት ወታደሮች ገዳ/ጀዲ በታኅሣሥ ወጥቶ 29 ዕለት ከ28 ኬክሮስ የሚታይ መልኩ እንደ ፍየል፡፡ ደላዊ በጥር ወጥቶ 29 ዕለት ከ41 ኬክሮስ የሚታይ መልኩ እንደ ውኃ መቅጃ ባልዲ፡፡ ሑት በየካቲት ወጥቶ 31 ዕለት ከ10 ኬክሮስ የሚታይ መልኩ እንደ ዓሣ ነው፡፡

ምልኤል ፡-

በመጸው የሰለጠነው ኮከብ ምልኤል ሲሆን በሥሩ ያሉት ሦስት ከዋክብት ሐመል በመጋቢት ወጥቶ 30 ዕለት ከ43 ኬክሮስ የሚታይ መልኩ እንደ በሬነው፡፡ ገውዝ/ጀውዝ በግንቦት ወጥቶ 31 ዕለት ከ30 ኬክሮስ የሚታይ መልኩእንደ ባልና ሚስት ጥንድ ነው፡፡

ሕልመልመሌክ፡-

በክረምት የሰለጠነው ኮከብ ሕልመልመሌክ ሲሆን በሥሩ ያሉት ከዋክብት/ወታደሮች ሰርጣን/ ድርጣን በሰኔ ወጥቶ 31 ዕለት ከ26 ኬክሮስ የሚታይ መልኩ እንደ ጎርምጥ ነው፡፡ አሰድ በሐምሌ ወጥቶ 31 ዕለት ከ10 ኬክሮስ የሚታይ መልኩ አንበሳ ሰንበላ በነሐሴ ወጥቶ 30 ዕለት ከ42 ኬክሮስ የሚታይ መልኩ እንደ እሸት ዛላ ነው ፡፡

በዚህ መነሻነት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የወቅት አቆጣጠር እንደሚከተለው ይገለጻል፡፡

  • የመጸው ወቅት ከመስከረም 26 ቀን እስከ ታኅሣሥ 25

  • የበጋ ወቅት ከታኅሣሥ 26 ቀን አስከ መጋቢት 25

  • የጸደይ ወቅት ከመጋቢት 26 ቀን እስከ ሰኔ 25

  • የክረምት ወቅት ከሰኔ 26 ቀን እስከ መስከረም 25 ቀን ሲሆኑ እነዚህን ወቅቶች በማወቅ ዘመኑን በመዋጀት ሥራው ድንቅ የሆነ አምላክ ይመሰገንበታል፡፡ ቤተ ክርስቲያንም ሥርዐት ሠርታ በጸሎቱ በማኅሌቱ በቅዳሴው ወዘተ. ትጠቀምበታለች፡፡

ቤተክርስቲያን ወቅቶች ሲፈራረቁ አዲሱን ወቅት ለመቀበል ምኅላ (ጸሎት) ታደርጋለች ፡፡ ለምሳሌ ምኅላ በአተ ክረምት (የክረምት መግቢያ ምኅላ) እንደየ ዕለቶቹ እየታየ ከሰኔ 12 እስከ ሰኔ 23 ቀን ምኅላ ይያዛል፡፡ ይኸውም መጪው ክረምት እግዚአብሔር የሚመሰገንበትና የሚዘንበው ዝናብ ጥሩ ምርት የሚያስገኝ እንዲሆን ነው፡፡

ቅዱስ ጳውሎስም በመልእክቱ እንደጻፈው “ምድርም ብዙ ጊዜ በርስዋ የወረደውን ዝናም ከጠጣች መልካም ፍሬ ለደከሙበት ላረስዋትም ብታበቅል ከእግዚአብሔር ዘንድ በረከት ትቀበላለች” ብሏል ዕብ.6፡7 ፡፡ ቅዱስ ዳዊትም ወአንተ ገበርከ አድባረ ወምድረ ኵሎ፡፡ ክረምተ ወሐጋየ ዘአንተ ፈጠርከ ወተዘከር ዘንተ ተግባረከ፡፡ አንተ የምድርን ዳርቻ ሁሉ ሠራህ በጋንም ክረምትንም አንተ አደረግህ።ይህን ፍጥረትህን አስብ። (መዘ 74፡፡17)

“ክረምት” በደስታ ተክለ ወልድ መጽሐፈ ሰዋሰው ወግስ በሚለው መጽሐፋቸው ሲፈታው ክረምት ከረመ ዝናም የዝናብ ወቅት በፀደይና በመጸው መካከል ያለ ክፍለ ዓመት ከሰኔ 25 እስከ መስከረም 25 ድረስ ያለው ወቅት ሲለው ቅዱስ ያሬድም በድጓው ወያስተዴሉ ክረምተ ለምድር ዘያበቁል ሣዕረ ውስተ አድባር ይለዋል፡፡

ጥዑመ ልሳን ካሳ ደግሞ “ክረምት” የሚለው ቃል ከርመ፣ ከረመ ከሚለው የግእዝ ቃል የተገኘ ሲሆን ትርጓሜውም ወርሃ ዝናም፣ ወርኃ ነጎድጓድ፣ ዘመነ ባሕር፣ ዘመነ ነጎድጓድ፣ ዘመነ አፍላግ፣ ዘመነ ጠል፣ ዘመነ ደመና፣ ዘመነ መብረቅ… ይሉታል፡፡ ዘመነ ክረምት/ የዝናብ ወቅት በዘጠኝ ይከፈላል አራቱ በሚጠናቀቀው ዓመት እስከ ጳጉሜ መጨረሻ ሲሆን አምስቱ ደግሞ በሚቀጥለው ዓመት ውስጥ በመስከረም ናቸው፡፡ በያዝነው ዓመት ውስጥ ያለው ክፍል ፡-

  1. ዘር፣ ደመና እስከ ሐምሌ 18 ቀን

  2. መብረቅ፣ ባሕር፣ ወንዞች እስከ ነሐሴ 9 ቀን

  3. እጓለ ቁአት ፣ደሰያት ፣የሁሉም ዓይኖች እስከ ነሐሴ 27

  4. ንጋት፣ቀን፣ፍጥረት በሚል እስከ ጳጉሜን 5 ወይም 6 ናቸው፡፡ እነዚህ አራት ጊዜዎች እንደ አንድ ይቆጠራሉ፡፡

የዝናብ/የክረምት ወቅት ቤተ ክርስቲያን እግዚአብሔርን በልዩ ሁኔታ የምታከብርበት ወቅት ነው፡፡

ቤተክርስቲያን እግዚአብሔር የሰማይና የምድር ፈጣሪ መጋቢ መሆኑን በዝናብ ምልክትነት /አስረጅነት ታስተምራለች፡፡ በግብርና የሚተዳደሩ የሀገራችን ሰዎች በክረምት የዘሩት ዘር ፍሬ የሚያፈራው በክረምት እግዚአብሔር በሚሰጠው ዝናብ ስለሆነ ቸርነቱ መጋቢነቱ በዚህ ይመሰላል፡፡

ድሃ ስንሆን ተስፋችንን በእግዚአብሔር ላይ እናደርጋለን እርሱ ዝናቡን ይሰጠናል፡፡ ዘር እግዚአብሔርን ተስፋ በማድረግ በአፈር ውስጥ ይቀበራል ዝናብ ሲያገኝ አድጐ ለፍሬ ይበቃል፡፡ ስለዚህ ከሰኔ 25 – ሐምሌ 18 ያለው ወቅት ዘርዕ ደመና ተብሎ መጻሕፍት ይነበባሉ፡፡ መዝሙሮች ይዘመራሉ፡፡

የሚቀርበው ምስጋና የዝናብን ወቅት እግዚአብሔር ሰጠን ምሕረትን አደረገልን ሰንበትን ለሰዎች ሠራልን ስለዚህ እርሱን ከፍ ከፍ እናድርገው እናመስግነው በማለት ነው፡፡ እንዲሁም ሰማዩን በደመናት ይሸፍናል ለምድርም ዝናብን ያዘጋጃል ሣርን በተራሮች ላይ ያበቅላል ለምለሙንም ለሰው ልጆች ጥቅም። በማለት ቤተክርስቲያን በቅዱስ ዳዊት ምስጋና ታመሰግነዋለች፡፡ መዝ 147፡8 ፡፡

በሐምሌ 2፣5፣20፣ 15 16 አሠርገዎሙ ለሐዋርያት እየተባለ ሐዋርያት በመዝሙር ይታሰባሉ፡፡ 2ጴጥ.1፡12-18 ሐዋ.23፡10-35 ከሐምሌ 19-ነሐሴ 9 መብረቅ ነጎድጓድ ባሕር አፍላግ ጠል እየተባለ ይዘመራል መጻሕፍት ይነበባሉ ፡፡ 1ጴጥ.2፡1-12፣ ሐዋ.20፡1-2፡፡

በዘመነ ክረምት ውኃ ይሰለጥናል፣ ውኃ አፈርን ያጥባል፣ እሳትን ያጠፋል፡፡ ሆኖም ግን በብሩህነቱ ከእሳት፤ በቀዝቃዛነቱ ከነፋስ፤ በእርጥብነቱ ከመሬት ጋር ተስማምቶ ከሦስቱ ባሕርያት ጋር ይኖራል፡፡ ይህ ዘመን ስለ ሥነ ፍጥረት ዘርዘር ባለ መልኩ የሚነገርበት ዘመን ስለሆነ ፍጡርን ከፈጣሪ መናን ከተመጋቢ ለይቶ የሚያሳይና የሚያሳውቅ ዘመን ነው፡፡

ወርኃ ክረምት የክርስትና ምሳሌ ነው፤ ገበሬ በወርሃ ክረምት ብርዱንና ዝናሙን ሳይሰቀቅ ለሥራ ይሰማራል፤ በበጋው የእጁን ፍሬ ያገኝ ዘንድ የክረምቱን መከራ ይታገሳል፡፡ ክርስቲያንም በዚህ ምድር ላይ የሚደርስበትን መከራ ሁሉ ይታገሳል፤ ክርስቲያንም በዚህ ምድር የሚደርስበትን መከራ ሁሉ በጸጋ የሚቀበለው በዚያኛው ዓለም ስለሚያገኘው ተድላና ደስታ ነው፡፡

ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ፡- “እለ ይዘርኡ በአንብዕ ወበኃሤት የአርሩ፡፡ ሶበሰ የሐውሩ ወፈሩ እንዘ ይበክዩ፡፡ ወፆሩ ዘርኦሙ፡፡ ወሶበ የአትዉ መጽኡ እንዘ ይትፌሥሑ፡፡ በሔዱ ጊዜ ዘራቸውን ተሸክመው እያለቀሱ ተሰማሩ፤ በተመለሱ ጊዜ ግን ነዶአቸውን ተሸክመው ደስ እያላቸው ይመጣሉ፡፡” በማለት የመንፈሳዊ ጉዞ ምሥጠርን ከግብርና ሙያ አንጻር አመልክቶአል፡፡(መዝ.125)

“ምድርን ጎበኘሃት አጠጣሃትም ብልፅግናዋንም እጅግ አበዛህ የእግዚአብሔር ወንዝ ውኃን የተሞላ ነው ከምድር ዳር ደመናትን ያወጣል፣ በዝናም ጊዜ መብረቅን አደረገ፤ ነፋሳቱንም ከመዛግብቱ ያወጣል ” (መዝ.64፥9) በማለት እግዚአብሔር በነጎድጓድና በመብረቅ በባሕርና በሐይቅ ሁሉ ላይ ሥልጣን ያለው አምላክ መሆኑንና የሚታዩና የማይታዩ ፍጥረታት ሁሉ የኃይሉ መገለጫዎች እንደሆኑ የሚያስተምሩ መዝሙራት ይዘመራሉ፡፡

እግዚአብሔር ክረምትን ሲያመጣና ዝናምን ሲያዘንም ብዙ ነገሮችን ልናስተውል ይገባናል፡፡ ፈጣሪያችን ፈጣሪ ዓለማት ብቻ ሳይሆን መጋቢ ዓለማት መሆኑን መረዳት ያሻል፡፡ መግቦቱም ከፍጥረቱ እንዳልተለየ ይህ አማናዊ መግቦቱም ፍጥረቱን እንደሚያስተምር እንረዳለን፡፡

በምድር ዘመን ሁሉ መዝራትና ማጨድ፤ ብርድና ሙቀት፤ በጋና ክረምት፤ ቀንና ሌሊት አይቋረጡም፡፡” (ዘፍ.8፥22) በማለት አምላካችን እግዚአብሔር ለኖኅ በገባለት ቃል ኪዳን መሠረት በጋና ክረምቱ ብርድና ሙቀቱ ቀንና ሌሊቱ በተወሰነላቸው ጊዜ እየተፈራረቁ ለሰው ልጆች ጥቅም እንዲሰጡ አድርጓቸዋል፡፡

በዚህ መሠረት ኢትዮጵያዊያን በአንድ ዓመት ውስጥ እየተፈራረቁ በሚመጡ አራት ወቅቶች ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ከቅዱሳት መጻሕፍት ምሥጢርና ምሳሌ ጋር በማስማማት ለየወቅቱና ለዕለታቱ ምንባባትን በማዘጋጀት እግዚአብሔርን ታመሰግናለች፡፡ ስለዚህ በክረምት ወቅት እግዚአብሔርን እያመሰገንን እንድናሳልፍ እግዚአብሔር ይርዳን፡፡

ይቆየን

  • ምንጭ :-ባሕረ ሐሳብ የዘመን ቆጠራ ቅርሳችን
mkgermany exhibition 2

ልዩ ዐውደ ርዕይ በጀርመን ፍራንክፈርት ከተማ ይካሔዳል

ሰኔ 25 ቀን 2006 ዓ.ም.

አውሮፓ ማእከል

mkgermany exhibition 2በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የማኅበረ ቅዱሳን የአውሮፓ ማእከል የጀርመን ቀጠና ማእከል “ለሁለንተናዊ የቤተ ክርስቲያን እድገት የድርሻችንን እንወጣ” በሚል መሪ ቃል ልዩ ዐውደ ርዕይ፤ ዐውደ ጥናትና የስብከተ ወንጌል መርሐ ግብር በፍራንክፈርት ከተማ ኢኮነን ሙዚየም ከሰኔ 27- 29 ቀን 2006 ዓ.ም./July 4-6, 2014/ እንደሚካሔድ ቀጠና ማእከሉ አስታወቀ፡፡

በዝግጅቱም የኢትዮጵያ ጥንታዊ ገዳማትና አብነት ትምህርት ቤቶች ታሪክ አስተዋጽኦና ወቅታዊ ሁኔታ፤ የቤተ ክርስቲያኒቱ እንቅስቃሴ በጀርመንና በአውሮፓ፤ የቅዱስ ያሬድ አጠቃላይ የዜማ ባሕል እና ሌሎችም ጥናታዊ ጽሑፎች ይቀርባሉ፡፡ በመርሐ ግብሩ ላይ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ በአውሮፓ ሀገራት የሚገኙ የማኅበሩ አባላትና ምእመናን ታዳሚ እንደሚሆኑ ይጠበቃል፡፡