a seltagn 2006 01

ከጠረፋማ አካባቢዎችና ከግቢ ጉባኤያት ለተውጣጡ ተተኪ መምህራን ሥልጠና እየተሰጠ ነው

 ሐምሌ 17 ቀን 2006 ዓ.ም.

እንዳለ ደምስስ

  • 850 የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ድቁና ተቀብለዋል፡፡

a seltagn 2006 01በማኅበረ ቅዱሳን የትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል አስተባባሪነት ከጠረፋማ ኣካባቢዎችና ከግቢ ጉባኤያት ለተውጣጡ ተተኪ መምህራን በአቡነ ጎርጎርዮስ የትምህርትና ሥልጠና ማእከል፤ እንዲሁም በስድስት ማእከላት ሥልጠና እየተሰጠ ይገኛል፡፡

አርባ ዘጠኝ ከተለያዩ ጠረፋማ አካባቢዎች የመጡ ተተኪ መምህራን ከሠኔ 30 ቀን 2006 ዓ.ም. ጀምሮ አዲስ አበባ በሚገኘው አቡነ ጎርጎርዮስ ትምህርትና ሥልጠና ማእከል ሥልጠናቸውን እየተከታተሉ ሲሆን፤ እስከ ሐምሌ 30 ቀን 2006 ዓ.ም. ይቆያሉ፡፡ በአንድ ወር ቆይታቸውም ትምህርተ ሃይማኖት፤ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፤ አምስቱ አዕማደ ምሥጢራት፤ ሐዋርዊ ተልእኮ፤ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ፤ ነገረ ቅዱሳን፤ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን፤ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንና ኦርቶዶክሳዊ መዝሙር በተሰኙ ርዕሶች ዙሪያ ሥልጠና እየወሰዱ ይገኛሉ፡፡

ከአርባ ዘጠኙ ሠልጣኞች መካከል ሁለቱ ቀሳውስት ሲሆኑ፤ ዐሥራ ሦስቱ ዲያቆናት ናቸው፡፡ ከጋምቤላ ክልል የመጣው ዲያቆን ቶንግ በሥልጠናው ገንቢ ዕውቀት ማግኘቱንና ከተለያዩ አካባቢዎች ከመጡት ሠልጣኞች ጋር ባለው ቆይታ ከፍተኛ የልምድ ልውውጥ ማድረጉን ገልጧል፡፡

ለሥልጠናው መሳካት የደብረ ኃይል ቅዱስ ራጉኤል ቤተ ክርስቲያን አንቀጸ ብርሃን ሰንበት ትምህርት ቤት የጎልማሶች ክፍል የስልሣ ሺህ (60,000) ብር ድጋፍ አድርጓል፡፡

በተመሣሣይ ሁኔታ ከግቢ ጉባኤያት ለተውጣጡ 361 ተተኪ መምህራን በስድስት ማእከላት በአሰላ (በኦሮምኛ ቋንቋ)፤ እንዲሁም በዝዋይ፤ በጅማ፤ በባሕር ዳር፤ በደቡብ ማስተባበሪያ (ሐዋሳ)፤ በማይጨው እና ከኬንያ ማእከል አንድ ሰልጣኝ ሥልጠናውን እየተከታተሉ ይገኛሉ፡፡

በተያያዘ ዜና ማኅበረ ቅዱሳን ኢትዮጵያ ውስጥ በሚገኙ ከ340 በላይ ዩኒቨርስቲዎችና ኮሌጆች ውስጥ ለሚገኙ ተማሪዎች የቤተ ክርስቲያን ትምህርት የሚሰጥ ሲሆን፤ በ2006 ዓ.ም. በግቢ ጉባኤያት የሚሰጠውን ትምህርት ካጠናቀቁ 40,000 ተማሪዎች ውስጥ 850ዎቹ ከብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የድቁና ማዕረግ ተቀብለዋል፡፡

 

erope teklala 2006 01

የአውሮፓ ማእከል ጠቅላላ ጉባኤ ተደረገ

 ሐምሌ 17 ቀን 2006 ዓ.ም.

በአውሮፓ ማእከል ሚድያና ቴክኖሎጂ ክፍል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ማኅበረ ቅዱሳን አውሮፓ ማእከል 14ኛ ጠቅላላ ጉባኤውን ከሐምሌ 11 እስከ 14 ቀን 2006 ዓ.ም. በኢጣልያ ዋና ማእከል ሮሜ ማእከል አካሄደ፡፡

erope teklala 2006 01በምእራብ አውሮፓ ልዩ ልዩ ሀገራት የሚገኙ ከሰማንያ በላይ አባላት፤ ከዋናው ማእከልና ከአሜሪካ ማእከል የተላኩ ልዑካን በተሳተፉበት ጉባኤ የማእከሉን የ2006 ዓ.ም. የአገልግሎት ሪፖርት ሰምቷል፤ የቀጣዩንም ዓመት ዕቅድና በጀት አጽድቋል፡፡ በተጨማሪም የማኅበሩ አገልግሎት በአኀጉሩ በሚፋጠንበት ዙሪያና በልዩ ልዩ አጀንዳዎች ላይ ተወያይቶ ውሳኔ አሳልፏል፡፡

በጉባኤው ላይ በሀገር ቤት እየተቸገሩ የሚገኙ ቅዱሳት መካናትንና አብነት ት/ቤቶችን ስለ መርዳት፣ በልዩ ልዩ ምክንያት ከሀገራቸው ተሰደው ያሉ ኢትዮጵያውያን ሊደረግላቸው ስለሚገባው መንፈሳዊ እርዳታ እና አውሮፓ ያለው የቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊ እንቅስቃሴ በሚፋጠንበት ሁኔታ ላይ የማኅበሩ አባላት ሊኖራቸው ስለሚገባቸው ድርሻ ትኩረት ከተሰጣቸው ጉዳዮች መካከል ይገኙባቸዋል፡፡ የጉባኤው ታዳሚዎች በቀረቡላቸው አጀንዳዎች ላይ ውይይት በማድረግ የውሳኔ ሐሳቦችንም አሳልፈዋል፡፡ በማኅበሩ መተዳደሪያ ደንብ መሠረትም የአገልግሎት ዘመኑን የፈጸመውን የማእከሉን ሥራ አስፈጻሚ በአዲስ ተክቷል፡፡

በጉባኤው ማጠቃለያ እንደተገለጠው የዘንድሮው ጠቅላላ ጉባኤ በእጅጉ የተሳካ እና በማእከሉ የጠቅላላ ጉባኤ ታሪክ ከፍተኛ ቁጥር ያለው ተሳታፊ የተገኘበት ሲሆን ዝግጅቱም በአግባቡ የተከናወነ እንደ ነበር የማእከሉ ሰብሳቢ ዲ/ን ሰሎሞን አስረስ ገልጸዋል፡፡

እንደ ሰብሳቢው ገለጻ «ጉባኤው የማእከሉን አገልግሎት በሚያጠናክሩና አባላት በያሉበት ኾነው በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ላይ ሊያደርጉት ስለሚገባው ተግባራዊ ሱታፌ እንዲወያዩ በማሰብ የተተለመ ነበር፡፡ አባለት በቀረቡላቸው የመወያያ ርእሰ ጉዳዮች ዙሪያ ጠቃሚ ውይይት በማድረግ ያሳለለፏቸው ውሳኔዎች ተግባራዊ እንዲኾኑ ክትትል ይደረጋል» ብለዋል፡፡

በጉባኤው አዘጋጅ ኮሚቴ በታቀደው መሠረት የጉባኤው ታዲሚዎች ሰኞ ሐምሌ 13 ቀን 2006 ዓ.ም በጋራ የጥንታዊቷን የሮሜ ከተማ ጎብኝተዋል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን በውጪው ዓለም አራት ማእከላትና ዐሥር ግንኙነት ጣቢያዎች ያሉት ሲሆን፤ የአውሮፓ ማእከል ከአራቱ ማእከላት አንዱ ነው፡፡ ቀጣዩ 15ኛ የማእከሉ ጉባኤ በፊንላንድ ዋና ከተማ ሄልሲንኪ እንዲከናወን ተወስኗል፡፡

 

kedus kerkos eyeleta

“መላእክት ሁሉ ረቂቃን አይደሉምን የዘላለም ሕይወትን ይወርሱ ዘንድ ላላቸው ለአገልግሎት ይላኩ የለምን” ዕብ.1፡14

 ሐምሌ 17 ቀን 2006 ዓ.ም.

kedus kerkos eyeleta

መላእክት እግዚአብሔር ሰማይንና ምድርን የሰማይንም ሠራዊት ፈጠረ በሚለው አንቀጽ እንደተጠቀሰው፤በመጀመሪያው ቀን በዕለተ እሑድ በእግዚአብሔር ቃል ተፈጥረዋል፡፡ እግዚአብሔር አፈጣጠሩ ድንቅ ነውና መላእክትን እንደ እሳትና ነፋስ የማይዳሰሱ የማይታዩ አድርጎ ፈጥሯቸው ያመሰግኑታል፡፡ ዘፍ.1፡1 መዝ.108፡4፣ ዕብ.1፡12

እግዚአብሔር የፈጠራቸው 20 ዓለማት ሲኖሩ ሦስቱ፤ ኢዮር፣ ራማ፣ ኤረር የመላእክት ከተሞች ናቸው፡፡

 

መላእክት በ30 ነገድ በ10 አለቃ ተከፋፍለው እግዚአብሔርን የሚያመሰግኑ ለፍጥረታት ሁሉ ምሕረትን የሚለምኑ ናቸው፡፡ 10ሩ ነገድ መኳንንት ይባላሉ፡፡ እነዚህ መላእክት ዓለትን ተራራን ሠንጥቀው የሚሄዱ፣ ቀስት መሳይ ምልክት ያላቸው፣ በትንሣኤ ዘጉባኤ ጊዜ ነፍስና ሥጋን የሚያዋሕዱ መላእክት ሲሆኑ አለቃቸው ሰዳክያል ይባላል፡፡

10ሩ ነገድ ሊቃናት ሲባሉ የእሳት ሠረገላ ያላቸው፣ ኤልያስን በሰረገላ የወሰዱት መላእክት ሲሆኑ አለቃቸው ሰላትያል ይባላል፡፡ 10ሩ ነገድ መላእክት ይባላሉ፡፡ ሕይወት የሌለውን ነገር ሁሉ በሥርዓት እንዲቆዩ የሚጠብቁ ሲሆኑ አለቃቸው አናንያል ይባላል፡፡ የኃይላት አለቃቸው ቅዱስ ሚካኤል ሲሆን የአርባብ አለቃቸው ደግሞ ቅዱስ ገብርኤል ነው፡፡

መላእክት ብርሃናዊ መልአክ ስለሆኑ የሚያግዳቸው የለም፡፡ አለት ተራራን ሰንጥቀው የመግባት አንዱ በአንዱ የማለፍ ችሎታ አላቸው፡፡ እንደ መብረቅ እንደ እሳት የመሆን ባሕርይ አላቸው፡፡

መላእክት ትጉኃን ናቸው፡፡

“መላእክት ሁሉ ረቂቃን አይደሉምን የዘላለም ሕይወትን ይወርሱ ዘንድ ላላቸው ለአገልግሎት ይላኩ የለምን” ዕብ.1፡14 እንዳለ እረፍታቸው ምስጋና ምስጋናቸው እረፍት ሆኖ ሌት ተቀን ይተጋሉ፡፡

መላእክት በእግዚአብሐር ፊት ይቆማሉ፡፡

መላእክት ለምሕረት በእግዚአብሐር ፊት ይቆማሉ፡፡ “በእግዚአብሔር ፊት የቆሙ ሰባት መላእክት አየሁ፡፡” ራዕ.8፡2፡፡እኔ በእግዚአብሔር ፊት የምቆመው ገብርኤል ነኝ ሉቃ.1፡19፣ ዘካ.1፡12 ፡፡
መላእክት ተራዳኢ ናቸው፡፡

ቅዱስ ዳዊት “የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙሪያ ይሰፍራሉ ያድናቸውማል” መዝ.33፡7፡፡ ሲል በዘፍ.48፡16 “ከክፉ ነገር የዳነን የእግዚአብሔር መልአክ እርሱ እኒህን ሕፃናት ይባርክ” በማለት ተራዳኢነታቸውንና በረከትን የሚያሳድሩ መሆናቸውን ያስረዳል፡፡ “ያን ጊዜም የጴጥሮስ ልቡና ተመልከትና እግዚአብሔር በዕውነት መልአኩን ልኮ ከሄሮድስ እጅና ከአይሁድ ሕዝብ ምኞት ሁሉ እንዳዳነኝ አወቅሁ አለ ሐዋ.12፡16፡፡ እነሆ ሚካኤል ሊረዳኝ መጣ ዳን.10፡13 ማቴ.18፡10 የመላእክትን ተራዳኢነት ያስረዳል፡፡

ጠባቂዎቻቸው ዘወትር የአባቴን ፊት ያያሉ፡፡

መላእክት ይጠብቁናል

በመንገድህ ሁሉ ይጠብቁን ዘንድ መላእክቱን ስላንተ ያዛቸዋልና እግርህም በድንጋይ እንዳትሰናከል በእጆቻቸው ያነሡናል” መዝ.90፡11-12፡፡ “ከነዚህ ከታናናሾቹ አንዱን እንዳትንቁ ተጠንቀቁ፤ መላእክቶቻቸው በሰማያት ዘወትር በሰማያት ያለውን የአባቴን ፊት ያያሉ እላችኋለሁና። ማቴ18፡10

“በመንገድህ ይጠብቅህ ዘንድ ወዳዘጋጀ ቤት ሥፍራ ያገንህ ዘንድ እነሆ አኔ መልአኩን በፊትህ እሰዳለሁ በፊቱ ተጠንቀቁ ቃሉንም አድምጡ ስሜም በእርሱ ስለሆነ ኃጢአት አትሥሩ ይቅር አይልምና አታስመርሩት ዘፀ.23፡20-22 መላእክት ዕጣንን ያሳርጋሉ፣ ራዕይ.5፡8፣ 8፣3 ፡፡ መላእክት የጸጋ ስግደት ይሰገድላቸዋል ዳን.5፡፡ኢያ.5፡13፣ ነገ.19፡6 15፣ ዘፍ.22፡3 መላእክት የምንመገበውን ይሰጡናል/ይመሩናል/ ት.ዳ.3 መላእክት ከእስር ያስፈታሉ ሐዋ.12፡6፡፡ መላእክት ይፈውሳሉ “እግዚአብሔር የበለዓምን ዐይን ከፈተ ዘሁ.22፡31

የመላእክትን አፈጣጠራቸውን፣አገልግሎታቸውን በመጠኑ ከተረዳን ከሰባቱ ሊቃነ መላእክት አንዱ የሆነው ቅዱስ ገብርኤል ሐምሌ 19 ቀን ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስና እናቱ ኢየሉጣን ያዳነበት፣የጸናናበት ለክብር ያበቃበትን ቀን በድርሳነ ገብርኤል የተገለጸውን እንዲህ አቅርበነዋል፡፡

ድርሳነ ገብርኤል ዘሐምሌ

በአገዛዝና በቅድምና ትክክል የሆነ፣ ከመታሰቡ አስቀድሞ ሁሉን መርምሮ የሚያውቅ፣ ክረምትን በየዓመቱ የሚያመጣ፣ ሰማይን በደመና የሚጋርድ፣ ምድርን በልምላሜ የሚሸፍናት፣ የባሕርን ውኃ በእፍኙ የሚለካ፣ ምድርን በስንዝሩ የሚመጥናት ከኛ ዘንድ ለሱ ምስጋና የሚገባው፣ ለኛ ሕይወትን የሚሰጠን አንድ አምላክ በሚሆን በአብ፣ በወልድ፣ በመንፈስ ቅዱስ ስም አምነን በሐምሌ 19 ቀን የሚነበብ የሚጸለይ የሰማያውያን አለቃ የሚሆን የቅዱስ ገብርኤል ድርሳን ይህ ነው፡፡

እለ እስክንድሮስ የተባለ መኰንን በኢየሱስ ክርስቶስ ያመኑትን ክርስቲኖች ለመቀጣትና ሌሎችም ፈርተው ክርስትናን እንዳይፈልጉ ለማድረግ አስቦ ሰም፣ ጨው፣ ባሩድ፣ ሙጫ፣ የዶሮ ማር፣ እርሳስ፣ ብረት፣ ቅንጭብ፣ ቁልቋል አንድ ላይ ተቀላቅሎ በብረት ጋን እንዲፈላ አዝዞ ነበር፡፡ ጭፍሮቹም እለስክንድሮስ እንዳዘዛቸው ከአደረጉ በኋላ ያዘዝኸንን ሁሉ ፈጽመን እሳቱ ነዶ ፈልቷል፤ ድምፁ እንደነጐድጓድ ይጮሃል፤ ወላፈኑም እንደ ፀሐይ ነፀብራቅ በሩቅ ይጋረፋል፤ የፍላቱም ኀይል አሥራ ዐራት ክንድ ያህል ከፍታ ወደላይ ይዘላል፤ እንግዲህ በውስጡ የሚጣሉትን እዘዝ አሉት፡፡

በዚህ ጊዜ ሕፃን ቂርቆስና እናቱ ኢየሉጣ በክርስቶስ ስም ስለሚያምኑ አሥረዋቸው ነበርና ከፍላቱ ሊጨምሯቸው ከእሥር ቤት አወጧቸው፡፡ ፍላቱ ወደ ላይ በሚዘል ብረት ጋን ውስጥ ለመጨመር ሲወስዷቸው የእነዚህን ቅዱሳን አሟሟት ያዩ ዘንድ በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ሰዎች እንዲሰበሰቡ ታዘዘ፡፡

በዚህ ጊዜ ቅድስት ኢየሉጣ የፍላቱን ጩኸት በሰማችና ባየች ጊዜ ተሸበረች፤ ተዘጋጅቶላት ከነበረውም ክብር ልታፈገፍግ ሞከረች፡፡

ልጅዋ ቅዱስ ቂርቆስ ግን እናት ሆይ ከዚህ የብረት ጋር ግርማ የተነሣ አትፍሪ፤ ድንጋፄም አይደርብሽ፤ አናንያንና አዛርያን፣ ሚሳኤልንም እግዚአብሔር ከዕቶነ አሳት እንዳወጣቸው ሁሉ እኛንም ከዚህ ከብረት ጋን ሊያወጣን ችሎታ ያለው መሆኑን አትጠራጠሪ ፡፡ እናት ሆይ ከዚህ ከሚያልፈው ዓለም ጭንቅና መከራ ለማዳን ስትይ በማያልፈው በዘለዓለም እሳት ለመቀጣት ትመርጫለሸን? ይህስ አይሆንም፤ ይቅርብሽ፤ በአሁኑ ጊዜ እግዚአብሔር በመካከላችን አለና ይረዳናል፡፡ እናቴ ሆይ ሶስናን ከእደ ረበናት፣ /መምህራነ አይሁድ/ ዳንኤልን ከአፈ አናብስት ያዳነ እሱ እኛንም ከዚህ የጋን ፍላት ያወጣናል፡፡ ይልቁንም እግዚአብሔር በዚህ የብረት ጋን ውስጥ ግዳጃችንን ልንፈጽም ፈቅዶ ከሆነ ኢዮብ ንብረቱንና ገንዘቡን፣ ልጆቹንና ሚስቱን፣ በመጨረሻም የተፈጥሮ አካሉን ባጣ ጊዜ እግዚአብሔርን አመሰግነዋለሁ፤ እግዚአብሔር ሰጠ፤ እግዚአብሔር ነሣ፤ /ወሰደ/ እግዚአብሔርም እንደ ወደደ አደረገ፤ ከማለት በስተቀር ምንም የተናገረው ክፉ ነገር እንደሌለ ሁሉ እኛም የሱን ዓላማ በመከተል ይህን መከራ ልንታገሥ ይገባናል፤ አላት፡፡

ነገር ግን እናቱ ቅድስት ኢየሉጣ በዚህ ምክር ልትጽናና ባለመቻሏ ቅዱስ ቂርቆስ ዓይኑን ወደ ሰማይ አቅንቶ አቤቱ አምላኬ ሆይ ይህችን ባሪያህን ከርስትህ የምትለያት ከሆነ ከባለሟልነትህ መጽሐፍ ፋቀኝ፤ አቤቱ አዝመራውን አቃጥለህ ፍሬውን ልትባርክ ትወዳለህን ይህን እንዳታደርግ ግን ቸርነትህ ትከለክልሃለች፡፡

አቤቱ እንጨቱን ቆርጣችሁ አንድዱት፤ ቅጠሉን ግን ጠብቁት፤ ብለህ ልታዝ መለኮታዊ ባሕርይህ አይደለም፤ ነገር ግን እንጨቱንም ቅጠሉንም ባንድ ጠብቁት፤ ብለህ ታዝዛለህ እንጂ፤ እንግዲህ በዚህ ምክንያት ይህን ያየ ሁሉ ማዳን የሚችል አምላክ ቢኖራቸውስ ኖሮ ከዚህ ከእሳት ባልሸሹም ነበር ብሎ አይጠራጠር፡፡

አቤቱ ዲያብሎስም ከባለሥልጣኑ ይልቅ እኔ በረታሁ፤ ቅዱሳኖቹንም ድል ነሣኋቸው፤ ብሎ እንዳይመካ ከመንጋውም አንድ በግ ቀማሁ፤ በማለት እንዳይደነፋ ለናቴ ጽኑ የሆነ ኃይለ መንፈስ ቅዱስን ስጣት፤ ብሎ በጸለየ ጊዜ ዲያብሎስ ከኢየሉጣ አጠገብ ብን ብሎ ጠፋ፡፡

ከዚህ በኋላ ቅድስት እናቱ በሰማያዊ መንግሥት አባት የሆንከኝ ልጄ ሆይ ጌታህ ኃይልን ሰጥቶኛልና የሚጠብቀንን ገድላችንን ፈጽመን ድል እናድርግ፤ እነሆ በብረት ጋኑ ውስጥ የሚነደውን እሳት በማይበት ጊዜ በለምለም /በምንጭ/ ላይ እንደሚወርድ ጠል ሆኖ አይቼዋለሁና አለችው፡፡

እኒህም ቅዱሳን ይህን በሚነጋገሩበት ጊዜ በውስጡ አንገትን የሚቆለምም፣ ልብን የሚያቀልጥ፣ ሆድን የሚሠነጥቅ፣ ሥርን የሚበጣጥስ መሣሪያ ካለበት የብረት ጋን ውስጥ ጨመሯቸው፡፡ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ገብርኤል ከሰማይ ወረደና የብረቱን ጋን እሳት አጠፋው፤ ከቅዱሳኑም አንዳቸውንም ሳያቃጥላቸው የብረቱ ጋን ማቃጠሉና መፍላቱም ፀጥ አለ፡፡

ወንድሞቻችን ሆይ እንግዲህ በጭንቃቸው ጊዜ ገድላቸውን እስኪፈጽሙ ድረስ ይህ መልአክ ከሰማዕታትና ከጻድቃን ጎን እንደማይለይ እወቁ፡፡ ለኃጥአንም ኃጢአታቸውን ይቅር ይላቸው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ይጸልይላቸዋል፡፡ እኛም የዚህን የሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል በዓሉን በየወሩ እያከበርን አማላጅና ወዳጅ እናድርገው፤ በዚህም በሚመጣውም ዓለም ሊረዳን ይችላልና፡፡

ዳግመኛም እለ እስክንድሮስ ሀሳቡ ሳይሳካለት ስለቀረ አሥራ አራት የሾሉና የጋሉ የብረት ችንካሮች አምጥተው ሰባቱን በእናቱ በኢየሉጣ አካል፣ ሰባቱን በቂርቆስ አካል ይቸነክሯቸው ዘንድ ጭፍሮቹን አዘዘ፡፡

ዳግመኛም የሕፃንን የእራስ ቆዳ ገፈው እሳት ውስጥ ይጨምሩት ዘንድ አዘዘ፡፡ አሁንም መልአኩ መጥቶ ይህን መከራ አራቀለት፡፡ ቀጥሎም በመቃን ውስጥ ጨምረው በገመድ እንዲጎትቱት አዘዘ፤ በዚህም ጊዜ መልአኩ አዳነው፡፡ ሕዝቡም ይህን ሁሉ ተአምር በአዩ ጊዜ እግዚአብሔርን አመሰገኑት፤ ቅዱስ ገብርኤልንም አከበሩት፡፡ እነዚህን ቅዱሳን ረድቶ ለክብር ያበቃ ቅዱስ ገብርኤል እኛንም በሃይማኖት ጸንተን ለክብር እንድንበቃ ይርዳን፡፡

የቅዱስ ገብርኤል፣የቅድስት ኢየሉጣና የቅዱስ ቂርቆስ በረከት አማላጅነት አይለየን፡፡

 

a gonder tabote 2006 02

የጎንደር መካነ ስብሐት ቅድስት ልደታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያን

ሐምሌ 16 ቀን 2006 ዓ.ም.

እንዳለ ደምስስ

ክፍል ሁለት

ጥምቀት

በጎንደር ጥምቀትን አስመልክቶ ታቦታት ከመንበራቸው ወጥተው ወደ ጥምቀተ ባሕር የሚወርዱበትና የሚመለሱበት ሦስት ዓይነት ሥርዓት ይገኛሉ፡፡ እነዚህም እየተፈጸሙ እስከ ዛሬ ድረስ ደርሰዋል፡፡

a gonder tabote 2006 02በዐፄ ገብረ መስቀል የነበረው ሥርዓት ታቦታት ከመንበራቸው ይወጣሉ፤ ወደ ጥምቀተ ባሕር ወርደው ሕዝቡን ባርከው በእለቱ ተመልሰው ወደ መንበራቸው ይገባሉ፡፡ በንጉሥ ላሊበላ ዘመን ደግሞ ቀድሞ የነበረው ሥርዓት ተቀይሮ ታቦታት ከመንበራቸው ወጥተው ወደ ወንዝ በመውረድ አድረው በመጡበት መንገድ እንዲመለሱ ተደረገ፡፡ ሦስተኛው በዐፄ ዘርዓ ያዕቆብ ዘመን የተጀመረ ነው፡፡ በዋዜማው ታቦታት ከመንበራቸው ወጥተው ወደ ጥምቀተ ባሕር በመውረድ ያድራሉ፡፡ አድረው ወደ መንበራቸው ሲመለሱ ግን ወደ ጥምቀተ ባሕር በወረዱበት ሳይሆን በሌላ መንገድ አገሩንና ሕዝቡን እየባረኩ እንዲመለሱ ተደረገ፡፡

ሦስቱንም ሥርዓት ዛሬ በጎንደር እንመለከታለን፡፡ የመጀመሪያው እንደ ዐፄ ገብረ መስቀል ሥርዓት ከመንበሯ ወጥታ ሕዝቡን ባርካ በዕለቱ ወደ መንበሯ የምትመለሰው የጎንደር በዓታ ለማርያም ናት፡፡ ከ2000 ዓ.ም. ጀምሮ ደግሞ ቅዱስ ኡራኤል በ22 ወጥቶ በእለቱ ሕዝቡን ባርኮ ወደ መንበሩ በክብር ይገባል፡፡ እንደ ዐፄ ላሊበላ ታቦታት ወጥተው ወደ ጥምቀተ ባሕር በመውረድ አድረው በመጡበት መንገድ መመለስን 8ቱ ዐፄ ፋሲል ባሰራው ጥምቀተ ባሕር የሚወጡት ታቦታት ናቸው፡፡ እንደ ዐፄ ዘርዓ ያዕቆብ ሥርዓት ታቦታት ወደ ጥምቀተ ባሕር በወረዱበት ሳይሆን በሌላ መንገድ ወደ መንበሯ የምትመለሰው ታቦት በጎንደር ውስጥ ብቸኛዋ የልደታ ለማርያም ታቦት ናት፡፡

መምህር ኤስድሮስ፡-

asdrose 2006 04በቤተ ክርስቲያኗ ከአንድ መቶ ሃምሳ በላይ የአቋቋምና የትርጓሜ መጻሕፍት መምህራን ነበሩባት፡፡ የአቋቋም መምህራንና ጉባኤው አሁንም ድረስ ሳይቋረጥ የቀጠለ ቢሆንም የትርጓሜ መጻሕፍት መምህራን ግን ድርቡሽ ቤተ ክርስቲያኗን ካወደመና ንዋያተ ቅድሳትን ዘርፎ ከፍተኛ ጉዳት አድርሶ ከሔደ በኋላ ወንበሩ እንደታጠፈ ነው፡፡ የመምህር ኤስድሮስ የትርጓሜ ወንበር ታጥፎ ወደ ሠለስቱ ምዕት ቤተ ክርስቲያን ተወስዷል፡፡

የጎንደር ልደታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያን ዐራት ዓይና የነበሩት መምህር ኤስድሮስ የትርጓሜ መጻሕፍትን ወንበር ዘርግተው በማስተማር ታላላቅ ሊቃውንትን ያፈሩባት ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ባለውለታ የሆነች ናት፡፡

መምህር ኤስድሮስ በልደታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያን የትርጓሜ መጻሕፍትን ጉባኤ ተክለው ወንበር ዘርግተው በማስተማር የተለያዩ የቤተ ክርስቲያንን መጽሕፍት እየመረመሩ ለተማሪዎቻቸው በቂ እውቀት እያስጨበጡ ተመርቀው ይወጣሉ፡፡ ከደቀመዛሙርቱም መካከል የቻለ ወንበር ዘርግቶ በማስተማር፤ ሌሎቹ ደግሞ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ማገልገላቸውን ይቀጥላሉ፡፡

በቤተ ክርስቲያናችን ሁለት ዓይነት የአተረጓጎም ሥልቶች ይገኛሉ፡፡ እነሱም የላይ ቤትና የታች ቤት ትርጓሜ በመባል ይታወቃሉ፡፡ የትርጓሜ መጻሕፍትን በምሥጢር ካበለጸጓቸው መምህራን አንዱ መምህር ኤስድሮስ ሲሆኑ፤ የታች ቤት ትርጓሜ መሥራችም ናቸው፡፡

መምህር ኤስድሮስ መጸሕፍትን በመመርመር የሚታወቁ በመሆናው አንድ ወቅት ወደ ጣና ገዳማት ሔደው ከ300 በላይ መጻሕፍትን ለማንበብ ችለዋል፡፡ መጻሕፍቱን በማንበባቸው ቀድሞ በነበራቸው እውቀት ላይ በመጨመር እስከዚያ ጊዜ ድረስ ለተማሪዎቻቸው ያስተማሩት ትምህርት በቂ እንዳልነበር ተረዱ፡፡ በዚህም ምክንያት ከዚህ ቀደም አስተምረዋቸው፤ ለወጡ ደቀ መዛሙርቶቻቸው መልእክት በመላክ “የጎደለን ምሥጢር አለ” በማለት እንዲሰበሰቡ አደረጉ፡፡

በርካቶቹ የመምህራቸውን ጥሪ ተቀብለው ቢመጡም፤ ጌታ ዮናስ የተባሉት ደቀመዝሙራቸውና ሌሎች ግን እርስዎ ልዩ ትርጓሜ ከመጨመርዎ በፊት አስተምረውናል በማለት በመምህር ኤስድሮስ ተሻሻለ የተባለውን አንድምታ ትርጓሜ ለመማር ፈቃደኛ ሳይሆኑ ቀርተዋል፡፡ እንደ ምክንያትነት ያስቀመጡት “ኢተወለድነ እምዝሙት፤ እኛ ከዝሙት አልተወለድንም፡፡ ከመጀመሪያው ጉባኤ ተምረን ተመርቀን ወጥተናልና አንመለስም” በማለታቸው ነው፡፡

ጥሪያቸውን ተቀብለው ለመጡት ደቀመዛሙርቶቻቸው ከጣና ገዳማት ከመጻሕፍት ያገኙትን እውቀት ሳይቆጥቡ ያላስተማሩትን እየጨመሩ ምሥጢሩን አስፋፍተው፤ ያጠረውን እያስረዘሙ፤ የረዘመውን እያሳጠሩ አስተማሯቸው፡፡

የመምህር ኤስድሮስን ጥሪ ተቀብለው በመምጣት እንደገና አስፋፍተው ያስተማሩትን “የታች ቤት ትርጓሜ” ሲባል፤ ጥሪያቸውን ሳይቀበሉ የቀሩትና እነ ጌታ ዮናስ በቀጣነት ያስተማሩት ጥንታዊው ትርጓሜ ደግሞ “የላይ ቤት ትርጓሜ” ተብሎ ለሁለት ተከፈለ፡፡ በአሁኑ ወቅትም በጎንደር ተስፋፍቶ የሚሰጠው የታች ቤት ትርጓሜ ሲሆን፤ በጎጃምና አካባቢው ደግሞ የላይ ቤት ትርጓሜ በስፋት እየተሰጠ ይገኛል፡፡ /የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ከልደተ ክርስቶስ እስከ 2000 ዓ.ም. ገጽ194፤ ዝክረ ሊቃውንት፤ በመልአከ ምክር ከፍያለው መራሒ፤ 2003 ዓ.ም./

አለቃ ገብረ ሃና፡-

aleka g 2006 01ከልደታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያን ጋር ተያይዞ ስማቸው ከሚነሱ ሊቃውንት መካከል አለቃ ገብረ ሃና አንዱ ናቸው፡፡ በዓታ ለማርያም ወንበር ዘርግተው አቋቋም እያስተማሩ ወደ ልደታ ለማርያም እየመጡም ያገለግሉ ነበር፡፡ አለቃ ገብረ ሃና ለልደታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያን አንድ ከበሮ ራሳቸው አሰርተው በስጦታ አስገብተው ስለነበር ወደ ቤተ ክርስቲያኗ በሚመጡበት ወቅት አገልግሎት ይሰጡበታል፡፡ እስከ ዛሬም ድረስ በልደታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያን የሚገኝ ሲሆን፤ “የአለቃ ገብረ ሃና ከበሮ” እየተባለም ይጠራል፡፡ ከበሮው በቅርስነት የተያዘና በክብር እንዲቀመጥ በመደረጉ ለዓመታዊ ክብረ በዓል ካልሆነ በቀር ለአገልግሎት አይወጣም፡፡

የድርቡሽ ጦር ጠባሳ፡-

የድርቡሽ ጦር በተለይም በጎንደር በሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት ላይ ያደረሰው ከፍተኛ ውድመት በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ውስጥ የራሱን ጠባሳ ጥሎ አልፏል፡፡ አባቶች ታርደዋል፤ ተሰደዋል፤ ንዋያተ ቅድሳት ተዘርፈዋል፤ ተቃጥለዋል፡፡ ከፍተኛ ውድመት ከደረሰባቸው አብያተ ክርስቲያናት መካከል አንዷ የልደታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡

ቤተ ክርስቲያኗን ድርቡሽ ከማፍረሱ በፊት ምን ትመስል እንደነበር መገመት ይከብዳል፡፡ ነገር ግን የንጉሥ ኢያሱ ዜና መዋዕል እንደሚነግረን “ዐፄ ዮስጦስ ልደታ ለማርያም የምትባል ረጅም ፤ ከፍ ያለች ፤ ከከፍታዋ የተነሳ ከርቀት የምትታይ ቤተ ክርስቲያን ሠሩ” እያለ ይነግረናል፡፡

ከልደታ ለማርም ቤተ ክርስቲያን ታሪክ ጋር ስማቸው ከሚነሱ ነገሥታት መካከል ዐፄ ዮስጦስ፤ ንጉሥ ዐጽመ ጊዮርጊስ፤ ንጉስ ተክለ ሃይማኖትና ዐፄ በካፋ ይገኙበታል፡፡ ቤተ ክርስያኗን በተለያዩ ዘመናት በማሠራት ይታወቃሉ፡፡

የዐፄ ዮስጦስ የንግሥና ዘመን በአጭርነቱ ከሚጠቀሱት ውስጥ የሚደመር ሲሆን፤ ለአምስት ዓመታት በንግሥና በቆዩባቸው ዘመናት በርካታ ቤተ ክርስቲያንና አገርን የሚጠቅሙ ሥራዎች ለመሥራት ጥረዋል፡፡ ነገር ግን በዙሪያቸው የነበሩ ተቀናቃኞቻቸው ሊያጠፏቸው ሌት ተቀን ያደቡ ስለነበር አባ እንጦንስ ቤተ ክርስቲያን ሔደው አስቀድሰው እንደተመለሱ ከምግብ ጋር መርዝ ሰጥተዋቸው የካቲት 12 ቀን 1708 ዓ.ም. አርፈው በማግሥቱ የካቲት 13 ቀን ሥርዓተ ቀብራቸው ተፈጽሟል፡፡ መቃብራቸውም በልደታ ማርያም ቤተ ክርስቲያንና በቤተልሔሙ መካከል ከቤተ ክርስቲያኑ ተጠግቶ ይገኛል፡፡ የልደታ ቤተ ክርስቲያንን ቅጥርና ደጀ ሰላም በማሠራት ላይ እያሉ በመሞታቸውም ዐፄ በካፋ ቅጥሩን አሠርተው አጠናቀውታል፡፡

በድርቡሽ ወራራ የልደታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያን ንዋያተ ቅድሳት ወደ ጣና ደሴቶች እንደተወሰዱ የሚነገር ሲሆን፤ የት እንዳሉ ግን ማወቅ አልተቻለም፡፡ ሳይወሰዱ የተረፉትም እንደ ብራና፤ ተአምረ ኢየሱስ፤ የደብሩን ታሪክ በተለይም የንጉሱን ታሪክ የሚናገር ስንክሳር የመሳሰሉት መጻሕፍት ዛሬም ድረስ በቤተ ክርስቲያኗ ይገኛሉ፡፡

ድርቡሽ በጎንደር ውስጥ በርካታ አብያተ ክርስቲያናትን አፍርሷል፤አቃጥሏል፤ ንዋየ ቅድሳትን ዘርፏል፡፡ ነገር ግን የድርቡሽ ጦር የልደታ ለማርያምና የቁስቋም አብያተ ክርስቲያናት ደጀ ሰላምን ማፍረስ ግን አልተቻለውም፡፡

አሁን ያለው ቤተ ክርስቲያን እንዴት ታነጸ?

amde kome 2006 03የልደታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያንን የቀድሞ ገጽታ ከፍርስራሹና ሙሉ ለሙሉ ካልወደቁት ቆመ ብእሲ በመነሳት መገመት አይቻልም፡፡ ድርቡሽ ቤተ ክርስቲያኗን ሲያወድም ቅጥሩን ግን ማፍረስ ሳይችል ቀርቶ እስከ ዛሬ ድረስ ከነደጀ ሰላሙ አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል፡፡ ቤተ መቅደሱ ውስጥ ያለው ግድግዳ የጥንቱ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያኗን ድርቡሽ ካፈረሰ በኋላ መቃረቢያ ተሰርቶላት ለረጅም ዘመናት በዚያ ሲቀደስ ነበር፡፡ ይህ አሁን አገልግሎት እየሰጠ ያለው ቤተ ክርስቲያን በ1970ዎቹ ውስጥ የታነጸ ነው፡፡

በወቅቱ ቤተ ክርስቲያኗን ያሠሩት በዓታ ለማርያም ሲያገለግሉ የነበሩ ቄስ አቡሐይ የሚባሉ አባት ናቸው፡፡ የቤተ ክርስቲያኗ ገጽታ እየፈረሰ መሆኑን በመረዳታቸው ምእመናንን ሰብስበው ላሰራው በማለት ጥያቄ አቀረቡ፡፡ በወቅቱ የነበሩት የቤተ ክርስቲያኗ አስተዳደርና ምእመናን ከለከሏቸው፡፤ እሳቸው ግን ተሰፋ ባለመቁረጥ አስተዳደሩንም ሆነ ምእመናንን ለማሳመን ባደረጉት ተከታታይ ጥረት ተፈቅዶላቸው አሳንጸዋል፡፡ በዚህ ወቅት በርካታ ፈተና ገጥሟቸዋል፤ ብዙም ደክመውበታል፡፡ የዓፄ ዮስጦስና የመምህር ኤስድሮስ ታላቅ ሥፍራ ፈርሶ መቅረት የለበትም በሚል በቁጭት ተነሣስተው ለፍጻሜ ለማብቃት ችለዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያኑን ማሠራት ብቻ ሳይሆን ለቤተ መቅደሱ ልዩ ድምቀት የሆኑትን ቅዱሳት ሥዕላትን በማሣል አስረክበዋል፡፡

 

aleka 2006 1

ሊቁ አለቃ ወልደ ሰንበት ተገኝ አረፉ

 ሐምሌ 15 ቀን 2006 ዓ.ም.

እንዳለ ደምስስ

aleka 2006 1የብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ፤ እንዲሁም በርካታ ጳጳሳትንና ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንን በማስተማር የሚታወቁት ሊቁ አለቃ ወልደ ሰንበት ተገኝ በተወለዱ በ99 ዓመታቸው ሐምሌ 8 ቀን 2006 ዓ.ም. አረፉ፡፡ ስርዓተ ቀብራቸው ለ35 ዓመታት ሲያገለግሉበት በነበረው ሽሮ ሜዳ መንበረ ስብሐት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን የቤተ ክርስቲያኗ ሊቃውንት፤ ቤተሰቦቻቸውና ምእመናን በተገኙበት ሐምሌ 9 ቀን 2006 ዓ.ም ከቀኑ 9፡00 ሰዓት ተፈጽሟል፡፡

አለቃ ወልደ ሰንበት ተገኝ ከሕፃንነታቸው ጀምሮ የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት በመማር፤ እንዲሁም ወንበር ዘርግተው በማስተማር በርካታ ሊቃውንትን በማፍራት ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን የቀሰሙትን እውቀት ለተተኪው ትውልድ በማስተላለፍ የበኩላቸውን ተወጥተዋል፡፡

በተለያዩ ቦታዎች በመማርና በማስተማር በርካታ ዓመታትን አሳልፈው ከ1971 ዓ.ም. ጀምሮ አዲስ አበባ ሽሮ ሜዳ በሚገኘው መንበረ ስብሐት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን እስከ እለተ እረፍታቸው ድረስ በመሪ ጌታነት ሲያገለግሉ ቆይተዋል፡፡አለቃ ወልደ ሰንበት ለስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 19ኛ ዓመት፤ ቁጥር 22/ ቅጽ 19፤ ቁጥር 254 ከነሐሴ 1- 15 ቀን 2004 ዓ.ም. እትም ለአብርሐም ቤት ዓምድ የሰጡትን ቃለ ምልልስ እንደሚከተለው አቀናብረነዋል፡፡

ሰኔ 16 ቀን 2004 ዓ.ም. “ዝክረ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልእ” የተሰኘ መርሐ ግብር በማኅበረ ቅዱሳን የጥናትና ምርምር ማእከል አስተባባሪነት በቀሲስ ሰሎሞን ወንድሙ ጥናት አቅራቢነት በኢትዮጵያ ቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለሥልጣን አዳራሽ ተካሒዶ ነበር፡፡ በመርሐ ግብሩ ላይ ከተገኙት ተጋባዥ እንግዶች መካከል አንድ አባት ላይ ዐይኖቼ አረፉ፡፡ የሀገር ባሕል ሙሉ ነጭ ልብስ ለብሰው፤ከላይ ጥቁር ካባ ደርበዋል፡፡ ጥቁር መነጽር አጥልቀው፤ ከዘራቸውን ተመርኩዘው በዕድሜ የበለጸገውን ሰውነታቸውን በጥንቃቄ እየተቆጣጠሩ፤ በቀስታ እግሮቻችን አንስተው እየጣሉ ወደ አዳራሹ ዘለቁ፡፡

ውስጤ ማነታቸውን በማወቅ ጉጉት ተወረረ፡፡ ይዟቸው የመጣው ወንድም ከመድረኩ ፊት ለፊት ካለው የመጀመሪያ ረድፍ ወንበር ላይ እንዲቀመጡ ረዳቸው፡፡ ተከትያቸው በመግባት ሲረዳቸው የነበረውን ወንድም ማንነታቸውን ጠየቅሁት፡፡ አንዲት ቁራጭ ወረቀት ከኪሱ አውጥቶ ሰጥቶኝ ወደ እንክብካቤው ተመለሰ፡፡

አነበብኩት፤ በአግራሞት እንደተሞላሁ ደጋግሜ ተመለከትኳቸው፡፡ በዕድሜ ገፍተዋል፤ በዝምታ ተውጠው የመርሐ ግብሩን መጀመር በትእግስት ይጠባበቃሉ፡፡ በአዕምሯቸው የተሸከሙት የዕውቀት ዶሴ ማን ገልጦ አንብቦት ይሆን? ለዘመናት ሲጨልፉት ከኖሩበት ከቤተ ክርስቲያን የዕውቀት ባሕር ለስንቱ አጠጥተው አርክተው ይሆን? ከሕሊናዬ ጋር ተሟገትኩ፡፡ ከዚህ በፊት ታላላቅ ቤተ መጻሕፍቶቻችን የተባሉት አባቶች ለገለጣቸው ሁሉ ተነበዋል፡፡ ለትውልድ ዕውቀታቸው ተላልፏል፤ በመተላለፍም ላይ ይገኛል፡፡ እኚህ አባት ከደቂቃዎች በኋላ የማጣቸው ስለመሰለኝ ውስጤን ስጋት ናጠው፡፡

መርሐ ግብሩ እንደተጠናቀቀ ቀረብ ብዬ ላናግራቸው ብሞክርም ለረጅም ስዓት ከመድረኩ የሚተላለፉ መልእክቶች ሲከታተሉ በመቆየታቸው ተዳክመዋል፡፡ ማነጋር አልቻልኩም፡፡ ነገር ግን የሚገኙበትን ደብር ማንነታቸው ከሚገልጸው ወረቀት ላይ ስላገኘሁ ተረጋጋሁ፡፡

ከቀናት በኋላ ታላቁን ሊቅ ሽሮ ሜዳ ከሚገኘው መንበረ ስብሐት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን አጠገብ ከሚገኘው መኖሪያ ቤታቸው አገኘኋቸው፡፡ በሕይወት ተሚክሯቸው ዙሪያም ቆይታ አደረግን፡-

ስምዐ ጽድቅ፡- ስለ ሕጻንነት ዘመንዎ ቢያጫውቱን?

አለቃ ወልደ ሰንበት፡- የተወለድኩት ዋድላ ደላንታ ሸደሆ ቅዱስ ሚካኤል አጥቢያ በዐፄ ምኒልክ ዘመን በ1907 ዓ.ም ነው፡፡ አባቴ ተገኝ፤ እናቴ ደግሞ እንደሀብትሽ ትባላለች፡፡ የሕፃንነት ዘመኔ አስቸጋሪ ነበር ማለት ይቻላል፡፡ በሕፃንነቴ ገና ዳዴ እያልኩ ነው ሁለቱም ዓይኖቼ ባልታወቀ ምክንያት የጠፉት፡፡ እናቴ እያለቀሰች ወደ እግዚአብሔር ከመጮኽ ሌላ ምርጫ አልነበራትም፡፡ አዝላኝ ትውላለች፤ ከጀርባዋ አታወርደኝም ነበር፡፡ በሀገራችን ታቦቱ ሰሚ የሆነ የቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን አለ፡፡ እዚያ ይዘሽው ሔደሽ ለምን አታስጠምቂውም፤ ከዳነልሽ የታቦቱ አገልጋይ ይሆናል ተብላ ወሰደችኝ፡፡ ወዲያውኑ አንደኛው ዓይኔ በራልኝ፡፡ ሌላኛው ግን በድንግዝግዝ ነበር የሚያይልኝ፡፡ እናቴም በተደረገላት ተዓምራት በመደሰት ከከብቶቿ መካከል አንዱን ወይፈን ወስዳ ለቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ስዕለቷን ሰጠች፡፡ ብዙም ሳይቆይ ኩፍኝ ያዘኝና በድንግዝግዝ የነበረው አንዱ ዓይኔ ሙሉ ለሙሉ ጠፋ፡፡ አንዱ ብቻ ቀረ፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡– የቤተ ክርስቲያን ትምህርት አጀማመርዎ እንዴት ነበር?

አለቃ ወልደ ሰንበት፡- ለቤተ ክርስቲያን የተለየ ፍቅር በውስጤ ያደረው ገና በሕፃንነቴ ነው፤ ወደ ትምህርቱም አደላሁ፡፡ የተማርኩት ብዙ ቦታ ነው፡፡ ዙር አምባ ቅዱስ ያሬድ ካስተማረበት ቦታ ጀምሮ ከብዙ መምህራንም እውቀት ቀስሜአለሁ፡፡ ከየኔታ ክፍሌና ከየኔታ ተካልኝ ጽጌ ምዕራፍ፤ ድጓ፤ ጾመ ድጓ፤ ዝማሬ መዋዕስት ተምሬአለሁ፤ አቋቋምም ከእነሱ ሞካክሬአለሁ፡፡ ለአቋቋም ልዩ ፍቅር ነበረኝ፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡– አቋቋምን ከማን ተማሩ?

አለቃ ወልደ ሰንበት፡- አቋቋም የነፍሴ ምግብ ሆኖ ይሰማኛል፡፡ ከዜማ ይልቅ ወደ አቋቋም አዘነበልኩ፡፡ ደብረ ታቦር መልአከ ገነት ጥሩነህ ዘንድ አምስት ሆነን አቋቋም ለመማር ገባን፡፡ እሳቸው በየቦታው የሚያገኟቸውን የአቋቋም አይነቶችን ተምረዋል፡፡ የጎንደር ቀለም ግን እዚያ አይቆምም፡፡ እኔም ሁሉንም ለመማር ጥረት አድርጌአለሁ፡፡ ነገር ግን ሲያስተምሩን የጎንደርን የታች ቤትንና የተክሌን አደበላለቁብን፡፡ ለምን እንዲህ ይሆናል ብዬ አምስት ዓመት ከእሳቸው ጋር ከቆየሁበት ጥዬ በመውጣት አለቃ መንገሻ ዘንድ ሔድኩ፡፡

አለቃ መንገሻ ዘንድ ለሁለት ወራት ደጅ ስጠና ቆየሁ፡፡ ከሁለት ወራት ቆይታ በኋላ አስጠርተውኝ ከየት እንደመጣሁ፤ የት እንደተማርኩ ጠይቀውኝ ሁሉንም ነገርኳቸው፡፡ በመጨረሻም ፈቅደውልኝ የአቋቋም ትምህርቴን ቀጠልኩ፡፡ በተለይም የላይ ቤት፤ የተክሌ አቋቀቋም ላይ ትኩረት ሰጥቼ ተማርኩ፡፡ ከአለቃ መንገሻ ዘንድ ለአስራ ሰባት ዓመታት ተቀምጫለሁ፡፡ ዝማሬ መዋስዕት፤ ድጓ፤ ጾመ ድጓንና ሌሎችንም ለተማሪዎች አስተምር ነበር፡፡ ቅኔ ከሦስት ሊቃውንት ነው የተማርኩት፡፡ ከአለቃ ብሩ፤ ከአለቃ መጽሔትና የአቋቋም ተማሪዬ ከነበረው ሊቀ ጠበብት ወልደ ሰንበት ተምሬአለሁ፡፡እኔ አቋቋም እያስተማርኩት እሱ ደግሞ ቅኔ አስተምሮኝ ተመረቅሁ፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- ወንበር ዘርግተው ማስተማሩን እንዴት ጀመሩ?

አለቃ ወልደ ሰንበት፡- መምህሬ አለቃ መንገሻ ከአዲስ አበባ ከሚገኘው በዓታ ለማርያም እንዲመጡ ጥሪ ተደርጎላቸው ስለነበር አብረን እንድንሔድ ቢጠይቁኝም እምቢ በማለት ጸናሁ፡፡ የሚቀረኝን ትምህርት ለመማር ስለፈለግሁ ዙር አምባ ወፋሻ ኪዳነ ምሕረት የእድሜ ባለጸጋ ከነበሩት አባት ዘንድ ሃያ አምስት ሆነን ለመሔድ ተስማምተን መልእክት ሰደድንላቸው፡፡ እሳቸውም ጥያቄአችንን ተቀበሉን፡፡

አለቃ መንገሻ በድምጼ በጣም ይገረሙ ስለነበር ጨጨሆ ላይ ብታዜም ዋድላ ደላንታ ይሰማል ይሉኝ ስለነበር “መድፉ”፤ “ወልደ ነጎድጓድ” በማለት ይጠሩኛል፡፡ በአቋሜ እንደጸናሁ ስለተረዱም “ልጄ አብረን ብንሆን መልካም ነበር፤ ይቅናህ” በማለት ግንባሬን ስመው አሰናበቱኝ፡፡ ዙር አምባ ኪዳነ ምሕረት የተወሰነ ጊዜ ከቆየሁ በኋላ በደብረ ታቦር አጋጥ ኪዳነ ምሕረት ወንበር ዘርግቼ አቋቋም ማስተማር ጀመርኩ፡፡

ደብረ ታቦር እያለሁ ዐሥራ ሦስት የሚደርሱ አብያተ ክርስቲያናት መምህር ስላልነበራቸው እየተዟዟርኩ አገልግያለሁ፡፡ ነገር ግን ከተወሰኑ ጊዜያት በኋላ ያንን አካባቢ ተውኩና ጋይንት ልዳ ጊዮርጊስ ለማስተማር ወረድኩ፡፡ እልም ያለ በረሃ ነው፡፡ ጥቂት እያስተማርኩ ቆይቼ ተማሪዎቹ በረሃውን መቋቋም እየተሳናቸው ጥለውኝ ሔዱ፡፡ በዚህ ሁኔታ መቀጠል ባለመቻሌ በ1941 ዓ.ም. ወደ ዳውንት ሔድኩ፡፡ ዳውንት ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን እስከ 1945 ዓ.ም. ተማሪዎችን ሰብስቤ ወንበር በመዘርጋት አቋቋም፤ ዝማሬ መዋስዕት፤ ድጓ፤ ጾመ ድጓ ማስተማሬን ቀጠልኩ፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- ከብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልእ ጋር እንዴት ተገናኛችሁ?

አለቃ ወልደ ሰንበት፡– በ1943 ዓ.ም. ተከስተ ብርሃን /ተከስተ ብርሃን የሚለው ስያሜ አለቃ ወልደ ሰንበት ያወጡላቸው ስም ነው፡፡ መምህራን ተማሪዎቻቸውን በምግባራቸውና በትምህርት አቀባበላቸው ተነስተው ስም ማውጣት የተለመደ ነው፡፡/ ዳውንት ቅዱስ ጊዮርጊስ ከማስተምርበት መጣ፡፡ ታዲያ እርሱና የአሁኑ ዝዋይ ሐመረ ብርሃን ቅዱስ ገብርኤል ገዳም አበምኔት አባ ሐረገ ወይን ጸናጽሉ ቢቀላቸውም ዘንጉ ይከብዳቸው ነበር፡፡ ተከስተ ብርሃን የሚለውን ስያሜ ያወጣሁለት በወቅቱ በነበረው የትምህርት አቀባበል ፍጥነቱንና ኃይለኛነቱን ተመልክቼ ነው፡፡በትምህርት እርሱ ዘንድ ቀልድ የለም፡፡ ተማሪዎቼ ሲያለምጡ የሚገስጻቸው እርሱ ነበር፡፡

ተከስተ ብርሃን ለትምህርትና ለሥራ ልዩ ፍቅር ነበረው፡፡ ፈቀደ /መቂ የደብረ አለቃ ሆኖ ነበር አሁን ግን አርፏል/ ከሚባል ተማሪ ጋር ሆነው “ተማሪው በትርፍ ጊዜው እየተንጫጫ ለምን ያስቸግራል፤ ለምን እርሻ አናርስም፤ በማለት ሃሳብ አቅርበው ዶማና መጥረቢያ ፈልገው ተማሪውን ሰብስበው ጫካውን እየመነጠሩ በበሬ አረሱት፡፡ ምሥር ዘርተውበት ሃምሳ ቁምጣ አስገብተዋል፡፡

በተጨማሪ ከቤተ ክርስቲያኑ በላይ በኩል ዳገታማ ሥፍራ ላይ ተማሪውን አስቆፍረው ገብስ ዘሩበት፡፡ “እባካችሁ ተማሪውን በሥራ እያማረራችሁ አታፈናቅሉብኝ” እላቸዋለሁ፡፡ እነሱ ግን ሦስት ኩንታል ገብስ አምርተው አስገቡ፡፡ ከትምህርታቸው በተጓዳኝ ጥጥ ገዝተው እያመጡ ለአካባቢው ሴቶች እያስፈተሉ ጋቢና ኩታ ያሰሩ ነበር፡፡ ተዉ ብላቸውም አሸነፉኝ፡፡ ተማሪ ሥራ ሲፈታ ስለማይወዱ ነበር ይህንን የሚያደርጉት፡፡

በተለይ ተከስተ ብርሃን ተማሪዎቹን ስለሚገስጽ ተማሪዎቹ “ይኼ ጥቁር ፈጀን እኮ” እያሉ ስሞታ ያቀርባሉ፡፡ እኔም ጠባዩን ስላወቅሁት “አንድ ስህተት አግኝቶባችሁ ይሆናል እንጂ ያለ ምክንያት አይቆጣችሁም” እያልኩ ፊት አልሰጣቸውም ነበር፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- እርስዎ ምን አይነት መምህር ነበሩ?

አለቃ ወልደ ሰንበት፡- እኔም ኃይለኛ ነበርኩ፡፡ ተማሪዎቼ ሲያጠፉ በኃይል ነበር የምገርፋቸው፡፡ አስቸጋሪ ተማሪ ካጋጠመኝም አባርራለሁ፡፡ ይህን የማደርገው ለእውቀት ከፍተኛ ፍቅር ስለነበረኝ የእኔን አርአያነት እንዲከተሉ ለማድረግ እንጂ በክፋት አልነበረም እርምጃውን የምወስደው፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- ለተማሪውና ለእርስዎ ድርጎ ከየት ያገኙ ነበር?

አለቃ ወልደ ሰንበት፡- ቀዳማዊ ዐፄ ኃይለ ሥላሴ ለተማሪዎች አቡጀዲና ለቀለብ የሚሆን ገንዘብ ይልኩልኛል፡፡ “የኢትዮጵያ መድፏና መትረየሷ ጸሎት ነው” በማለት በጸሎት እንድንበረታ መልእክት ይሰዱልኛል፡፡ እኔም በታማኝነት የቻልኩትን ሁሉ አደርግ ነበር፡፡ በተጨማሪም ዋድላ ደላንታ ላይ የተሰጠኝ እስከ ሠላሳ ጥማድ የሚያሳርስ የእርሻ መሬት ነበረኝ፤ የተመረተውን አስመጥቼ ለተማሪዎቼ ቀለብ አደርገው ነበር፡፡ ተማሪዎቼም የለመኑትን ያመጣሉ፤ በዚህ ሁኔታ ችግራችንን እንወጣ ነበር፡፡
ስምዐ ጽድቅ ፡- ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ እርስዎ ዘንድ ለምን ያህል ጊዜ ቆይተዋል?

አለቃ ወልደ ሰንበት፡– ተከስተ ብርሃን ለሁለት ዓመታት አቋቋም ካስተማርኩት በኋላ ነው የተለያየነው፡፡ ከዚያ በኋላ የት እንዳለ ሳላውቅ በደርግ ዘመን ጵጵስና መሾማቸውን ሰማሁ፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- ስለ ቤተሰብዎ ጥቂት ቢያጫውቱን

አለቃ ወልደ ሰንበት፡– በ1947 ዓ.ም. ነው ትዳር የመሠረትኩት፡፡ ስምንት ልጆችን ወልጃለሁ፡፡ አራቱ አርፈዋል፡፡ የልጅ ልጆችም አሉኝ፡፡ አንዱ የልጅ ልጄ ደሴ መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ቅኔ ቤት ገብቶ እየተማረ ነው፡፡ ለአባቱ ያሉኝን መጻሕፍት ልስደድለት እለዋለሁ፡፡ እሱ ደግሞ ቆይ ይደርሳል እያለኝ ነው፡፡ አያቴ ገብረ ተክሌ የታወቁ የድጓ መምህር ነበሩ፤ እኔም የእሳቸውን ፈለግ ተከትያለሁ፡፡ በተራዬ እኔን የሚተካ ከልጅ ልጆቼ መካከል በመገኘቱ ተደስቻለሁ፡፡ የቤተ ክርስቲያንን ሓላፊነት ይሸከም ዘንድ ተገኘልኝ፡፡ እግዚአብሔር መጨረሻውን ያሳምርለት፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- አዲስ አበባ እንዴት መጡ?

አለቃ ወልደ ሰንበት፡- ባለቤቴም አረፈች፡፡ እመነኩሳለሁ ብዬ ደብረ ሊባኖስ ገብቼ ነበር፡፡ የእግዚአብሔር ፈቃድ ስላልነበር አልተሳካልኝም፡፡ ሔኖክ የሚባል አቋቋም ያስተማርኩት ልጅ ደብረ ሊባኖስ አግኝቶኝ በ1971 ዓ.ም. አዲስ አበባ ሽሮ ሜዳ መንበረ ስብሐት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ወስዶ በመሪ ጌትነት እንዳገለግል አደረገ፡፡ እስከ ዛሬ ድረስ በዚሁ ቤተ ክርስቲያን እያገለገልኩ ቆይቻለሁ፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡– በቅርብ የሚረዳዎት ሰው አለ?

አለቃ ወልደ ሰንበት፡- የመጨረሻዋ ልጄ ከእኔው ጋር ናት፤ እግዚአብሔር እሷን አጠገቤ አኖረልኝ፡፡ እኔም ሰውም እየመረቅናት ነው፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡– ካስተማሯቸው ተማሪዎችዎ ማንን ያስታውሳሉ?

አለቃ ወልደ ሰንበት፡- ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ፤ ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል /የቀድሞው/ ዝዋይ የነበሩት፤ ብፁዕ አቡነ አትናቴዎስ /አሁን የወልዲያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤ በርካታ የደብር አለቃ የሆኑ ሊቃውንትን አፍርቻለሁ፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡– የሚያስተላልፉት መልእክት ካለዎት?

አለቃ ወልደ ሰንበት፡- እኔ የጋን ውስጥ መብራት ሆኜ ነው የኖርኩት፡፡ ተደብቄ ነው ያለሁት፡፡ ቅንነት መልካም ነገር ነው፤ ለሰው ልጅ እጅግ ያስፈልጉታል፤ ኖሬበታለሁም፡፡ ዕድሜና የሰው ፍቅር ሰጥቶኛል፤ ለእናንተም ይስጣችሁ፡፡ ከተደበቅሁበት አስታውሳችሁኛልና አምላከ ጎርጎርዮስ የማኅበሩን አገልግሎት ይባርክ፡፡ አሜን፡፡

 

 

gebi 2006 1

ማኅበረ ቅዱሳን ከ40,000 በላይ የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎችን አስመረቀ

 ሐምሌ 15 ቀን 2006 ዓ.ም.

እንዳለ ደምስስ

ማኅበረ ቅዱሳን በመላው ኢትዮጵያ በሚገኙ ዩኒቨርስቲዎች ትምህርታቸውን ሲከታተሉ የነበሩ ከ40,000 በላይ የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎችን አስመረቀ ፡፡

gebi 2006 1ማኅበረ ቅዱሳን ካሉት 46 የሀገር ውስጥ ማእከላት መካከል በ38ቱ ማእከላት አስተባባሪነት በዩኒቨርስቲ ቆይታቸው የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን መንፈሳዊ ትምህርት ሲከታተሉ የነበሩ ተማሪዎች አብዛኛዎቹ ዩኒቨርስቲዎች ከፍተኛውን ውጤት በማስመዝገብ የዋንጫና የሜዳልያ ተሸላሚ ሆነዋል፡፡ ከዩኒቨርስቲ ትምህርታቸው በተጓዳኝ መንፈሳዊ ዕውቀትን እንዲገበዩ በማድረግ ወደ ሥራ በሚሰማሩበትም ወቅት ራሳቸውን በመንፈሳዊውም በዓለማዊው ዕውቀት አዳብረው፤ በሥነ ምግባር ታንጸው ቤተ ክርስቲያንና ሀገራቸውን በታማኝነት እንዲያገለግሉ እንደሚረዳቸው በርካታ ተመራቂ ተማሪዎች ይገልጻሉ፡፡

የወልዲያ ዩኒቨርስቲ ለመጀመሪያ ጊዜ ካስመረቃቸው 250 ተማሪዎች መካከል 50ዎቹ የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች ሲሆኑ፤ ከእነዚህም ውስጥ 17ቱ በማዕረግ የተመረቁ ናቸው፡፡ በአምቦ ዩኒቨርስቲ የወሊሶ ካምፓስ በከፍተኛ ማዕረግ ተመርቀው የሜዳልያ ተሸላሚ ከሆኑት 6ቱ ተመራቂዎች ውስጥ 4ቱ የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች መሆናቸውን ከየማእከላቱ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡ በተጨማሪም የወልቂጤ ዩኒቨርስቲ ሁለት ትምህርት ክፍሎችን ብቻ በዚህ ዓመት የሚያስመርቅ ሲሆን፤ ከሚመረቁት 70 ተማሪዎች መካከል 14ቱ ከፍተኛ ማዕረግ የሚመረቁ የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች ሲሆኑ ከ1-3 በመውጣትም የሜዳልያና የዋንጫ ተሸላሚዎች ናቸው፡፡ በተያያዘ ዜና ከደብረ ብርሃን ዩኒቨርስቲ ከተመረቁት ተማሪዎች መካከል ከ7 ዮኒቨርሲቲዎችና ኮሌጆች 3 የወርቅ ሜዳሊያ 2 ዋንጫ ያገኙት የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች ናቸው፡፡ 

 

ክረምት

 ሐምሌ 15 ቀን 2006 ዓ.ም.

ካለፈው የቀጠለ

ከሐምሌ 19 እስከ ነሐሴ 21 ቀን ድረስ ያለው መካከለኛ ክረምት በመባል ይታወቃል፡፡ የክረምት ኃይልና ብርታት እንዲሁም ክረምትን ጥግ አድርገው የሚከሰቱ የተፈጥሮ ኃይላት ዑደት ያጸናበታል፡፡\ የዕለቱ ቁጥርም 33 ዕለት ነው፡፡ በዚህ ጊዜ መብረቅ፣ ነጎድጓድ ባሕርና አፍላግ ይሰለጥናሉ፡፡

መብረቅ የአምላክን ፈጣንነት፣ ነጎድጓድ የግርማውን አስፈሪነት፣ ባሕር የምሕረቱን ብዛት የሚያመለክቱ የእግዚአብሔር ባሕርይ ምሳሌዎች ናቸው፡፡ በዚህ ወቅት ጥልቆቹ የውኃ ቦታዎች መጠናቸው ያድጋል፣ የወንዞች ሙላት ይጨምራል፣ ምንጮች ይመነጫሉ፡፡ ሊቁ ቅዱስ ያሬድም “ዘይመይጦ ለመብረቅ ወያጸንኦ ለነጎድጓድ ዘርዋነ ያስተጋብዕ ወያበርህ ለመሃይምናን” /ድጓ ዘክረምት/ መብረቅን የሚመልሰው፣ ነጎድጓድን የሚያበረታው የተበታተኑትን ይሰበስባል፣ ለሚያምኑባትም ዕውቀትን ያድላል በማለት ብርሃንን ከምዕራብ ወደምሥራቅ እንደሚመልሰው ሁሉ መብረቅንም ካልነበረበት በጋ ወደሚኖርበት ክረምት የሚያመጣውና መገኛውን ደመና የሚፈጥርለት እርሱ ብቻ መሆኑን ያስረዳል፡፡

ፍጻሜ ክረምት

ፍጻሜ ክረምት ከነሐሴ 22 አስከ መስከረም 25 ያለው 39 ዕለት ነው፡፡ ይህ ሦስተኛው ክፍል በሁለት ይከፈላል፡፡ አንደኛው ዕጓለ ቋዓት፣ ደሰያት፣ ዐይነ ኲሉ ይባላል፡፡ ሁለተኛው ክፍል ደግሞ ብርሃን፣ ጎህ፣ ነግህ፣ ጽባሕ በመባል ይታወቃሉ፡፡

ከነሐሴ 22 እስከ ነሐሴ 29 ቀን ድረስ ያሉት ዕለታት ውስጥ ሕይወት ያላቸው ፍጥረታትና በባሕር የተከበቡ ደሴቶች ይታወሳሉ፡፡ ዕጓለ ቋዓት ቁራን /የቁራ ግልገልን/ ሲያመለክት በሥነ ፍጥረት አቆጣጠርን ግን በክንፍ የሚበሩ አዕዋፍን ሁሉ ይወክላል፡፡

ቁራ ሲወለድ ያለ ጸጉር በሥጋው ብቻ ይወለድና ከጊዜ በኋላ ጸጉር ያወጣል፡፡ በዚህ ጊዜ እነዚህ ጥቋቁሮች አሞሮች እነርሱን ባለመምሰሉ ደንግጠው እናቱም አባቱም ጥለውት ይሸሻሉ፡፡ “እናቴና አባቴ ትተውኛልና እግዚአብሔር ግን ተቀብሎኛል” /መዝ.26፡10/ የሚለው የንጉሥ ዳዊት ቃል እናትና አባቱ ለጣሉትና ለጠሉት፣ ትተውት ለሞቱበት ሰው ብቻ ሳይሆን እንዲህ ዓይነት ድርጊት በሚፈጽመባቸው ሕያዋን ፍጥረታት ሁሉ በአምላክነቱ የሚያደርግላቸውን ርኅራኄ የሚያሳይ ቃል ነው፡፡ በዚህ ጊዜ የሚከባከበው የሚመግበው ሲያጣ እግዚአብሔር በረድኤት አፍን ከፍቶ ምግብ ሲሻ ተሕዋስያንን ብር ብር አያደረገ ከአፉ ያስገባለታል፡፡ እዮብ “ልጆቹ ወደ እግዚአብሔር ሲጮኹ የሚበሉትም አጥተው ሲቅበዘበዙ ለቁራ መብልን የሚሰጠው ማን ነው” ብሏል /ኢዮብ 38፡41/፡፡ ቁራው እግዚአብሔር የሚሰጠውን እየተመገበ ቆይቶ ሲጠነክር እንደ እናትና አባቱ ያለ ፀጉር ያወጣል፣ በዚህን ጊዜ እናትና አባቱ መጥተው ይከባከቡታል፡፡

ደስያት ማለት በውኃ የተከበቡ ጠባብ ቦታዎች ማለት ነው፡፡ ለምሳሌ ኖኅ መርከብ ለፍጥረት መብዛት ምንጭ የሆኑ ነፍሳትን እንደያዘች ሁሉ አንዲት ደሴትም በውስጧ ብዙ ፍጥረታትን ትይዛለችና፡፡ ደሴት የኖኅ መርከብ ያረፈችበት የዓራራት ተራራ ምሳሌ ናት፡፡ እንዲሁም ከደሴያት የተጠጉ ድኅነትን እንደሚያገኙ ሁሉ በጥምቀት አማካኝነት ወደ ቤተ ክርስቲያን የተጠጉ ሁሉ ከሞት ሥጋና ከሞተ ነፍስ የሚጠብቃቸው የነፍሳቸውን እረኛ ኢየሱስ ክርስቶስን ያገኛሉና ደሴት የቤተ ክርስቲያን ምሳሌ ናት፡፡
ዓይን /ዓይነ ኲሉ፣ የሁሉ ዓይን/ የተጠቀሰው ሥጋዊ ዓይንን ለማመልከት ሳይሆን “ገንዘብህ ባለበት በዚያ ልብህ ይሆናል” /ማቴ.6፡21/ እንደተባለ የሥጋንም ሆነ የነፍስን ፍላጎት ለማሟላት የሚረዳ የሕሊና መሸትንና የመንፈስ ስብራትን የተመለከተ ፈቃደ መንፈስ ነው፡፡ “ልብ ካላየ ዓይን አያይም” እንዲሉ፡፡ /መዝ.136፡25/ ለሥጋ ምግብን የሚሰጥ “የሁሉ ዓይን አንተን ተስፋ ያደርጋል አንተም ምግባቸውን በየጊዜው ትሰጣቸዋለህ” መዝሙረኛው እንዳለ፡፡ ቅዱስ ያሬድም “ውኃውን በደመና አቁማዳ ይቋጥራል፣ ነገር ግን ደመናውን አይቀደድም፡፡ በዚህ መጋቢነት የሁሉ ነፍስ ዓይን እርሱን ተስፋ ያደርጋል” አለ፡፡ የእግዚአብሔር ቸርነቱን እያሰብን ሳንታክት ወደ እርሱ ብንመለስ እርሱ ወደ እኛ ይመለሳል፣ ብንለመነውም ይሰጠናል በማለት ሊቁ ተናግሮአል፡፡

ከላይ ያየነው ፍጻሜ ክረምት የመጀመሪያው ክፍል ሲሆን ሁለተኛው ክፍል የሚባሉት ብርሃን፣ ጎህ፣ ነግህ፣ ጽባሕ ይባላሉ፡፡ ቅዱስ ያሬድ በድርሰቱ ስለብርሃን ተፈጥሮና የሥራ ባሕርይ አስመልክቶ “ዘአንተ ታመጽእ ርእየቱ ብርሃን ወፈለጥከ ብርሃነ ለአዝማን ወለጊዜያት፣ የብርሃንን ወገግታ የምታመጣው አንተ ነህ ዘመናትንና ጊዜያትን በብርሃን ማእከላዊነት የለየሃቸውም አንተ ነህ” /ድጓ ዘክረምት/ በማለት ሊቁ እንዲል፡፡

ድጓ ዘክረምት “እስመ ብርሃን ሠረቀ ሎሙ” እግዚአብሔርን መፍራት እንድታውቅ በጠዋት ፀሐይ፣ በነግህ ብርሃን ይወጣልሃል እንዲሁም ሆኖ ብርሃን ወጥቶአልና ሰው ወደ ሥራው ተሠማርቶ እስኪመሽ ድረስ ይውላል እንዲል ቅዱስ ያሬድ፡፡

ማጠቃለያ

በዚህ አጭር ጽሑፍ ሙሉ የቅዱስ ያሬድን ትምህርት መግለጽ ባይቻልም ለቅምሻ ያህል ቅዱስ ያሬድ በዘመነ ክረምት አስተምሮቱ ምን እንደሚመስል ተመልክተናል፡፡ ይህ ዘመን ጠልና የልምላሜ የዘርና የቡቃያ ጊዜ በመሆኑ ከቅጠል በቀር በምድር ላይ ከወደቁት ዘሮች አብዛኛው ፍሬ አይገኝባቸውም፡፡ ዘመኑ ለመንግሥተ ሰማያት ያልተዘጋጀ፣ የንስሐ ፍሬ ያላፈራ ሰው ምሳሌ ነው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሸሽታችሁ በክረምት /ሞታችሁ ያለመልካም ሥራ/ እንዳይሆን ተግታችሁ ጸልዩ ያለው በደላችንን ባለማወቅ ለንስሐ ሕይወት ሳንበቃ በለጋነት ዕድሜያችን የምንሞተው ሞት አሳዛኝ መሆኑን ሲገልጽ ነው፡፡ ሊቁ በዚህ ክረምት /ዘመናችን/ ገና በቅጠል /ያለ ሥራ/ ሳለን ሽሽታችን /ሞታችን/ ያለፍሬ አይሁን በማለት ቅዱስ ያሬድ ድርሰቱን ከወንጌሉና ከዘመኑ ጋር በማጣጣም አስቀምጦልናል፡፡

 

፲ቱ ማዕረጋት

ሐምሌ 14 ቀን 2006 ዓ.ም.

መምህር ደጉ ዓለም
የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ
የሐዲስ ኪዳን መምህር

  • ኩኑ ቅዱሳን እስመ ቅዱስ አነ” ዘሌ.19፡2

ቅዱሳን ማለት የተቀደሱ፣ የከበሩ፣ የተመሰገኑ፣ የተለዩ፣ የተመረጡ፣ ንጹሐንየሆኑ፣ የጠሩ….. ወዘተ ማለት ነው፡፡ ቅዱሳን በዚህ ስም የሚጠሩበት ከሰው ወይም ከምድራዊ ባለሥልጣን የተቸሩት አይደለም፡፡

በሃይማኖት ጸንተው በምግባር ጐልምሰው የሥጋ ምኞታቸውን ጥለው አፍርሰው ሲገኙ የቅድስና ባለቤት ቅዱስ እግዚአብሔር እነሱን /ቅዱሳንን/ መሣሪያ አድርጐ ኃይሉንና ሥልጣኑን ቢገልጽባቸው ማኅደረ እግዚአብሔር መሆናቸው ይገለጻል፡፡ በዚህ ጊዜ ቅዱሳን ይባላሉ፡፡ እሱ እግዚአብሐር ቅዱስ ተብሏልና የጌትነቱ መገለጫ የሆኑ ሁሉ ቅዱሳን ይባላሉ ጻድቃን እንደመ ላእክት ውሉደ እግዚአብሔር ይባላሉ /ኢዮ.1፡6/፣ ሮሜ.8፡14/ ቅዱሳን ጻድቃን በግብር መላእክትን መስለው ሆነው የፈጣሪአቸውን ፈቃድ ፈጽመው በመገኘታቸው ከዚህ ዓለም በመለየታቸው ቅዱሳን ሲባሉ የፈጣሪአቸውን ሕያው መንግሥት ወራሾች ናቸውና ውሉደ እግዚአብሔር ይባላሉ፡፡ በሌላም ቃል ውሉደ ብርሃን ይባላሉ፡፡ /ሉቃ.16፡8/ በዓለማቸው ይራቀቃሉና ይህን ዓለም ይጠሉታል፡፡ ውሉደ ሕይወት ይባላሉ ሞትንና የሞት ከተማ ይህን ዓለም ይንቃሉና በክብር ተነሥተው ዳግመኛ ሲሞቱ የማይገባቸው ስለሆነ /ሉቃ.10፡30/ ውሉደ ጥምቀት ተብለዋል ሀብተ ወልድና ስመ ክርስትናን ተጐናጽፈዋልና፡፡ ውሉደ መንግሥትም ተብለዋል የመንግሥተ ሰማያት ባለቤቶች ናቸውና፡፡ በጸጋ እግዚአብሔር የበለጸጉ በመሆናቸው የእግዚአብሔር አዕይንተ እግዚአብሔር ተብለዋል /መዝ.33፡15/

የፈጣሪአቸው ፈቃድ በተግባራቸው ስለሚታይ የእግዚአብሔር አዝነ ፈቃድ ወደ ጻድቃን ነው፡፡ ልመናቸው ጾማቸው እንዲሁም ምጽዋታቸው ሁሉ የተወደደ መሥዋዕት ነው፡፡ ቅዱሳን በዓላማቸው ጾምን ግብዣ /ድግስ/፣ ለቅሶን ዘፈን፣ ደስታን ሐዘን አድርገው በመኖራቸው ይህ ተለዋዋጭ ዓለም በየጊዜው የሚአቀርብላቸው መርዶ በእነሱ ዘንድ ዋጋ የለውም ወይም ዋጋ አይሰጡትም፡፡ ዓለምም ለእነሱ የሚያቀርበው ዓለማዊ የምኞት ስጦታ እንደ ኢምንት የተቆጠረ ነው፡፡ የእግዚአብሔር ገጸ መዓቱ ወደ ዓለማውያን ሰነፎች እንደሆነ ገጸ ምሕረቱ ወደ ቅዱሳን ነው፡፡ ስለዚህ አማላጅነታቸው ጸሎታቸው በጣም ጠቃሚ ነው፡፡ “አፍቅርዎ ለእግዚአብሔር ኲልክሙ ጻድቃኑ” ቅዱሳን እውነትን ይዛችሁ ትሕትናን ተላብሳችሁ እግዚአብሔርን ውደዱት “እስመ ጻድቅ የሐስስ እግዚአብሔር” እግዚአብሔር እውነትን ትሕትናን ይወዳልና፡፡ /መዝ.30፡23/ የቅዱሳን ፍሬ ትሕትና ነው፡፡ በዓይነ ሕሊናቸው ፈጣሪአቸውን በዓይነ ሥጋቸው የእነሱን ምንነት እንዲሁም የዓለምን ከንቱነት ይመለከታሉ፡፡

 

ፍሬ የያዘ ተክል ሁሉ ቁልቁል የተደፋ ነው፤ ትሕትናን ያስተምራል፣ የጻድቃን ምሳሌ ነው፡፡ በፈሪሃ እግዚአብሔር ልቡ የተሰበረ እሱነቱን /ምንነቱን/ የመረመረ ሰው በዓይነ ሕሊናው የፈጣሪውን ቸርነት በዓይነ ሥጋው የራሱን ውድቀት ይመለከታል፡፡ ይህ አመለካከት ለጸጋ እግዚአብሔርና ለፍሬ ክብር ያደርሱታል፡፡ በመቅረዝ ላይ ያለች መብራት መሰወር እንዳይቻላት የመቅረዙ ከፍታ የግድ እንደሚገልጻት በተራራ ላይ ያለች ቤትም በእይታ እንደማትሰወር የተራራው ከፍታ እንደሚገልጻት በጥበበ እግዚአብሔር ከብረው በጸጋ እግዚአብሔር ተውበው የሚኖሩ ቅዱሳን ጻድቃንም ደረጃ በደረጃ ማዕረጋትን አልፈው ከመለኮት ባሕርይ ተካፍለው የተአምራት መገለጫ ተካፍለው የተአምራት መገለጫ ይሆናሉ፡፡ “መንክር እግዚአብሔር በላዕለ ቅዱሳኑ” /መዝ.67፡35/ “እግዚአብሔር በቅዱሳኑ በወዳጆቹ አድሮ የሚሠራው ሥራ ድንቅ ነውን፡፡ /2ኛጴጥ.1፡3/ ቅዱሳን የጸጋ ተዋሕዶ ተዋሕደው ሲገኙ ሙት ሲሆኑ ሙታንን ማስነሳት እውር ሲሆነ እውርን ማብራት፣ በዓለም ላይ ድንቅ ሥራቸው ይሆናል፡፡ የጸጋና የክብር ተሸላሚዎች ሆነዋልና በዓለም ላይ ሳሉ የሚመጣባቸውን ፈተና ሁሉ ከምንም ባለመቁጠር ተቋቁመው የጸጋ መቅረዝ ተቋሞች ይሆናሉ፡፡ በዚህም በአላሰለሰው ሕይወታቸው የአንበሳ አፍ ዘጉ /ዳን.7፡1-28/ ውኃውን ወደ ኋላው መለሱ /ዘጸ.14፡22/ ሰማይን አዘዙ /1ኛ ነገ.17፡1፣ ያዕ.5፡17/ ነበለባለ እዥሰት አበረዱ /ዳን.3፡1-13/ የአብርሃም የይስሐቅ የያዕቆብ ወዳጅ እግዚአብሔር ከዘመድ ባዕድ ከሀገር የሚኖሩትን በረድኤት ይቀበላል፣ ሥጋዊ ሀገረ ተድላን ጥለው ሓላፊ ጠፊ ምድራዊ ምቾታቸውን ንቀው ጸጋውን የሚጠባበቁትን ሁሉ አብሮአቸው ይኖራል፡፡ ትዕግስትን የጥዋት ቁርስ የቀን ምሳ የማታ እራት አድርገው የሚመገቡትን ሁሉ ቤተ መቅደስ አድርጓቸው ይገኛል፡፡ 

 

ቅዱሳን በዚህ ዓለም ይጠበቡበታል፣ ወጥተው ወርደው እነሱነታቸውን ከስስት ኃጢአት ጠብቀው ለወዲያኛው ዓለም ደግሞ በትዕግሥት ደጅ ይጠኑበታል፡፡ “አሪሃ እግዚአብሔር ትፍስህተ ልብ ውእቱ ወይሁብ ሐሴተ ወያስተፌስህ ወያነውሀ መዋዕለ ሕይወት፤ እግዚአብሔርን መፍራት የልብ ደስታ ነው፡፡ ፍጹም የሥጋና የነፍስን ደስታ ይሰጣል በሕይወትም ያኖራል፡፡” “ለፈሪሃ እግዚአብሔር ይሴኒ ድሐሪቱ ወይትባረክ አመ እለተ ሞቱ እግዚአብሐርን የሢፈራ ሰው ፍጻሜው ያምርለታል እንደ ኢዮብ ከደዌው ተፈውሶ ልጅ ልጅ አይቶ ይሞታል /ኢዮብ.31፡16/ ይህ ሁሉ በረከት የቅዱሳን የሁልጊዜ ፍሬ ነው፡፡

 

ቅዱሳን ሁል ጊዜ የሚሠሩት ሰማያዊ ድርብ ድርብርብ /እንደ ሐመረ ኖኅ/ በጸጋ ላይ ጸጋ እየተጨመረላቸው ወደ 10ሩ መእረጋት ይወጣሉ፡፡ በያዙት ቀን መንገድም ኢዮባዊ ትዕግስት አብርሃማዊ ሂሩት ይስሐቃዊ ፈቃደኛነት ያዕቆባዊ ቅን አገልግሎት ጠሴፋዊ ሀዳጌ በቀልነት ሙሴአዊ ለወገን ተቆርቋሪነት እየጨመሩ በመኖራቸው ሳያውቁት የፈጣሪአቸውን ኃይል የጌትነቱ የመለኮትነቱን ድንቅ ሥራ መገለጫዎች ይሆናሉ፡፡

ማዕረጋቸውን ከዚህ ይናገሩታል፡-

የንጽሐ ሥጋ ማዕረጋት 3 ናቸ ው እነሱም፡-

  1. ጽማዌ

  2. ልባዌ

  3. ጣዕመ ዝማሬ ይባላሉ፡፡

የንጽሐ ነፍስ ማዕረጋት 4 ናቸው

  1. አንብዕ

  2. ኲነኔ

  3. ፍቅር

  4. ሁለት ናቸው፡፡

የንጽሐ ልቡና ማዕረጋት ናቸው እነሱም

  1. ንጻሬ መላእክት

  2. ተሰጥሞ

  3. ከዊነ እሳት ናቸው፡፡

የንጽሐ ሥጋ ማዕረጋት

  1. ማዕረገ ጽማዌ፡- ይህ ማዕረግ የመጀመሪያው ነውና ማስተዋል ውስጣዊ ትዕግስትን ውስጣዊ ትህትና ውስጣዊ የራስ ሚዛንን ይዞ ማሰላሰል…… ወዘተ ይጀምራል፡፡ ከዚህ ማዕረግ ሲደርሱ እግዚአብሔርን ብቻ መዘከር ይችሉ ዘንድ የዚህን ዓለም ውጣ ውረድ ከማውራት ይከለከላሉ፡፡ በዚህ ማዕረግ መላእክት ሲወጡና ሲወርዱ ያያሉ፡፡ ነገር ግን ለምን እንደሚወጡና እንደሚወርዱ አያውቁም፡፡ ዮሐንስ ሐጺር የሰፋውን ስፌት ገበያ ላይ ለመሸጥ ተቀምጦ እያለ እርሱ ግን በተመስጦ እነ ቅዱስ ሚካኤልንና ቅዱስ ገብርኤልን እንዲሁም ሌሎችን መላእክት በየማዕረጋቸው እያየ ሲያደንቅ ስፌቱን የሚገዛ ሰው ቁሞ እንቅቡ ዋጋው ስንት ነው ብሎ ሲጠይቀው እርሱ የሚያየውን የሚያይ መስሎት “ሚካኤልኑ የዓቢ ወሚመ አኮ ገብርኤል ሚካኤል ይበልጣል ወይስ ገብርኤል” ብሎ በአንክሮ ጠየቀው፡፡ ይህን ሲለው ሰውየው ይሄስ እብድ ነው ብሎ ትቶት ሄዷል፡፡

  2. ማዕረገ ልባዌ፡– ደግሞ ማስተዋል ልብ ማድረግ አሰሙኝ እንጂ ስሙኝ አለማለት ልማር እንጂ ላስተምር አለማለት የተነገረው ትንቢትና ተግጻጽ ምዕዳን ሁሉ የራሱ እንደሆኑ መገመት መመርመር ዓይነ ሥጋን ከመጽሐፍ ከስነ ፍጥረት ዓይነ ነፍስን ከምስጢር….. ወዘተ ማዋል ነው፡፡ ወይም የእግዚአብሔርን ቸርነት ማድነቅ ስለሰው ያደረገውን ውለታ ማሰላሰል ከሰማየ ሰማያት መውረዱን ከሰው መወለዱን በገዳም መጾሙን መገረፉን ሥጋውን መቁረሱን ደሙን ማፍሰሱን መሰቀሉን መሞቱን መቀበር መነሳቱን እያሰቡ ልብን በፍቅረ እግዚአበሔር መሰበር አንደበትን በመንፈሳዊ ሕይወት መስበር ዓላማን በገጸ መስቀል/ትዕግሥት/ ማስተካከል የመሳሰሉት ናቸው፡፡

  3. ማዕረገ ጣዕመ ዝማሬ፡- ከዚህ ደረጃ ሲደርስ አንደበትን ከንባብ ልቡናን ከምስጢር ማቆራኘት ነው፡፡ ቅዱሳን ከዚህ ማዕረግ ሲደርሱ አንደበታቸው ምንም ዝም ቢል በልባቸው ውስጥ ዝም አይሉም፡፡ ከአፍ እስትንፋስ ከአፋፍ ላይ ነፋስ እንደማይለይ ሁሉ ከአንደበታቸው ትዕግስት ከእጃዋው ምጽዋት ከልቡናቸው ትሕትና ከሰውነታቸው ንጽሕና አይለይም፡፡

  4. የሚጸልዩትና የሚይነቡት ምስጢሩ እየገባቸው ስለሚያደርጉት አይሰለቻቸውም፡፡ ከዚህ ማዕረግ የደረሰ አንደ ባሕታዊ ለብዙ ዘመናት አቡነ ዘበሰማያት /አባታችን ሆይ/ እያለ ብቻ ሲኖር መልአክ መጥቶ ይትቀደስ ስምከ በል እንጁ ቢለው ኧረ ጌታዬ እኔስ አቡነ የሚለው ኃይለ ቃል ምስጢሩና ጣዕሙ በአፌ እንደ ጨሙ እየሟሟ አልጠገበኝ ብሏል እንዴት አድርጌ ወደፊት ልሂድ ብሎታል፡፡

የንጽሐ ነፍስ ማዕረጋት 

  1. ማዕረገ አንብዕ፡- ከዚህ ማዕረግ ሲደርሱ ቅዱሳን እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰው ልጅ ያደረገውን ፍቅር እስከ ሞትና መቃብር የተጓዘውን የመከራ ጉዞ እያሰቡ በአንጻሩም ምረረ ገሃነመ እሳትን ጣዕመ መንግሥተ ሰማያትን እያሰላሰሉ ውሉደ አዳም ይህን ሁሉ መከራ ባለ መገንዘብ ወደ ሰፊው የፈቃደ ሥጋ ሲጓዝ በማየታቸው ሲአለቅሱ ይታያል፡፡ ያለምንም መሰቀቅ ሲአለቅሱ እንባቸው እንደ ምንጭ ይፈሳል፡፡ እንደ ሰን ውኃ ይወርዳል ይኸውም ለዚህ ዓለም ብለው የሚአለቅሱት ልቅሶ ፊትን ያንጣጣል ዓይንን ይመልጣል የቅዱሳን ልቅሶ ግን ፊትን ያበራል ኃጢአትን ያስወግዳል እርጥብ እንጨት ከእሳት ጋር በተያያዘ ጊዜ እንጨቱ ከነበልባለ እሳት ሲዋሐድ እንጨቱ እርጥብነቱን ትቶ ውኃውን በአረፋ መልክ እያስወገደ ይነዳል፡፡ ቅዱሳንም በግብር/በሥራ/ ከመለኮት ጋር ሲዋሐዱ የዚህ ዓለም ምስቅልቅል ሥራ በሰማያዊ የረጋ ሕይወት ተለውጦ አሠራራቸው አካሄዳቸው ፍጹም ሕይወታቸው መልአካዊ ይሆናል፡፡

  2. ማዕረገ ኲነኔ፡- ከዚህ ማዕረግ ላይ ሲደርሱ ሥጋዊ ፈቃድ ሁሉ ለነፍስ ፈቃድ ይገዛል ነፍስ በሥጋ ባሕርያት ላይ ትሰለጥናለች ምድራዊ /ሥጋዊ/ ምኞት ሁሉ ይጠፋና መንፈሳዊ /ነፍሳዊ/ ተግባር ሁሉ ቦታውን ይወርሳል ያለምንም ማወላወል መንፈሳዊ ተግባር ሁሉ ይከናወናል፡፡

  3. ማዕረገ ፍቅር፡- ከዚህ ማዕረግ ሲደርሱ ውሉደ እግዚአብሔር ቅዱሳን እንደ ፈጣሪአቸው ሁሉን አስተካክለው በመውደድ ይመሳሰላሉ አማኒ መናፍቅ ኃጥእ ጻድቅ ዘመድ ባእድ ታላቅ ታናሽ መሃይም መምህር ሳይሉ አስተካክለው በመውደድ የእግዚአብሔር ልጆች መሆናቸውን ይገልጻሉ፡፡

  4. ማዕረገ ሁለት፡- ቅዱሳን ከዚህ ማዕረግ ላይ ሲደርሱ ባሉበት ሆነው ሁሉን ማየት መረዳት ይችላሉ፡፡ ጠፈር ደፈር ሳይከለክላቸው ርቀት ሳያግዳቸው ሁሉን በሁሉ ይመለከታሉ፡፡

የንጽሐ ልቡና ማዕረጋት

  1. ንጻሬ መላእክት

  2. ተሰጥሞ

  3. ከዊነ እሳት ናቸው፡፡

  1. ማዕረገ ንጻሬ መላእክት፡- ከዚህ ማዕረግ ሲደርሱ የመላእክት መውጣት መውረድ ማየት ተልእኮአቸውን ያለምንም አስተርጓሚ መረዳት ማነጋገርና ማማከር የመሳሰሉትን መፈጸም፤ ለምሳሌ እንደ ዮሐንስ አፈወርቅ መልአኩን 10 ዓመት ማቆም ነው፡፡

  2. ማዕረገ ተሰጥሞ፡- ከዚህ ማዕረግ ሲደረስ በባህረ ብርሃን መዋኘት ባሉበት ሆኖ ወደ ላይም ወደታችም መመልከት መቻል….. ወዘተ ናቸው፡፡

  3. ማዕረገ ከዊነ እሳት /ነጽሮተ ሥሉስ ቅዱስ/፡- የፈጣሪ ቤተ መቅደስ ሆኖ ጸጋ በተዋሕዶ ከመላእክት ጋር ሆኖ ረቆ ማመስገን ያሉበትን ሥጋ በብቻው ማየት በአካለ ነፍስ ሰማየ ሰማያትን መጐብኘት ገነት ውስጥ መግባት ናቸው፡፡

እነዚህም የቅዱሳን ማዕረጋት 10 ናቸው፡፡ /2ኛ ጴጥ.1፡4-10፣ ዮሐ.1፡40/ የአስሩ ማዕረጋት ምሳሌዎች የአስሩ ቃላት፡፡ /ዘጸ.20፡3-12፣ ዮሐ.13፡17/

በመጨረሻም ቅዱሳን የቅዱስ እግዚአብሔር ቤተ መቅደሶች ናቸው ኑሮአቸውም ቅዱስ ነው፡፡

የቅዱሳን በረከታቸው አይለየን፡፡ አሜን፡፡

  • ምንጭ፡- ዝክረ ቅዱሳን ኅዳር ፮ ቀን ፲፱፻፺፯ ዓ.ም.

የጎንደር መካነ ስብሐት ልደታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያን

ሐምሌ 10 ቀን 2006 ዓ.ም.

እንዳለ ደምስስ

ክፍል አንድ፡-

በጎንደር ከተማ በርካታ ጥንታውያን አብያተ ክርስቲያናት የሚገኙ ሲሆን አብያተ ክርስቲያናቱ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓትና ደንብ ጠብቀው፣ እንዲሁም በዘመኑ የነበሩ የኢትዮጵያዊያን የሥልጣኔ ደረጃ ከፍተኛ መሆንን የሚያመለክቱ አሻራዎች አርፎውባቸዋል፡፡ ይህንንም አሻራዎቻቸውን ይዘው ዛሬ ድረስ ዓለምን እያስደመሙ ይገኛሉ፡፡ እነዚህም አድባራትና ገዳማት በነገሥታት፤ በባላባቶችና በሀገሬው ሰው የተተከሉ ሲሆኑ፤ በነገሥታቱ ከተተከሉት አድባራት ውስጥ በ1703 ዓ.ም በንጉሡ በዐፄ ዮስጦስ የተመሠረተችው የጎንደር መካነ ስብሐት ልደታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያን አንዷ ናት፡፡

ደጀ ሰላሙ በድንጋይ ጥርብ እንደተካበ ጥንታዊነቱን ጠብቆ ግርማ ሞገሱን ተላብሶ ይታያል፤ የቤተ ክርስቲያኑ ዙሪያ በድንጋይ ካብ እንደታጠረ ከቅጥሩ ጋር ተያይዞ ነገሥታቱ ፀሎት ያደርጉባቸው የነበሩ በእንቁላል ቅርጽ የታነጹት ማማዎች ቁልቁል gonder ledetaአካባቢውን ለመቃኘት ያስችላሉ፡፡ ወደ ውስጥ ሲዘልቁ ድርቡሽ ጥንታዊውን ቤተ ክርስቲያን ሲያፈርስ ለታሪክ ምሥክርነት የቀሩት የቤተ ክርስቲያኑ ዓምዶች አሁን ያለውን ቤተ ክርስቲያን ዙሪያውን ከበው ይታያሉ፡፡ በግቢውና ውጪ የሚታዩት እድሜ ጠገብ ዛፎች፤ ቤተልሔሙ፤ የዐፄ ዮስጦስ መቃብር . . . ለቤተ ክርስቲያኑ ጥንታዊነት ምሥክርነታቸውን ይሰጣሉ፡፡

ግቢውን እየቃኘን በቤተ ክርስቲያኑ ዙሪያ ለመሥራት ላሰብነው ዘገባ መረጃ ሊሰጡን በቀጠሯቸው ተገኝተው እኛን በመጠበቅ ላይ ወደ ነበሩት አባቶችና ወንድሞች አመራን፡፡ ከቤተ ክርስቲያኗ አገልጋይ አባቶችና ወንድሞች ጋር ቤተ ክርስቲያኗን በሚመለከት ያደረግነውን ቆይታ እንደሚከተለው አጠናቅረነዋል፡፡

አመሠራረት

ዐፄ ዮስጦስ ንግሥናቸው በእናታቸው ወገን በመሆኑ በርካታ ተቀናቃኞች ነበሯቸው፡፡ ተቀናቃኞቻቸውም “ንግሥና በአባት ወገን እንጂ፤ እንዴት በእናት ወገን ይሆናል?” እያሉ በርካታ ሴራዎችን በማሴር ንግሥናቸውን ለመቀማት ጥረት አድርገውባቸው ነበር፡፡ ንጉሡ ግን ለእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የነበራቸው ፍቅር እጅግ ጥልቅ ከመሆኑ የተነሣ ተቀናቃኞቻቸውን በጦርነት ብቻ ሳይሆን በጾምና በጸሎት ድል ያደርጓቸው ነበር፡፡

በአንድ የጾመ ፍልሰታ ለማርያም ወቅት ሱባኤ ላይ እያሉ ከተቀናቃኞቻቸው መካከል አንዱ መንግሥታቸውን ለመቀማት ጦር አዘመተባቸው፡፡ ወታደሮቻቸው በሁኔታው በመደናገጥ “ከሱባኤዎ ይውጡ፤ የመጣውን የጠላት ጦር መክተን እንመልስ ዘንድ ይምሩን፤ በጠላት ከመያዛችን በፊት ድረሱልን” በማለት አስጨነቋቸው፡፡

ዐፄ ዮስጦስ ግን አሻፈረኝ በማለት ከያዙት ሱባኤ እንደማይወጡ ለወታደሮቻቸው ይናገራሉ፡፡ ወታደሮቻቸውም ጥያቄያቸውን በመቀጠል “በሚቀጥለው ዓመት ሱባኤ ይገባሉ፤ ራስዎን፣ እኛንም ለጠላት አሳልፈው አይስጡን፤ እባክዎ ከሱባኤ ወጥተው ጠላቶቻችንን ድል እናድርግ” በማለት ተማጸኗቸው፡፡

የወታደሮቻቸው ጉትጎታ አላሳርፍ ያላቸው ንጉሡ “ጠላትን ድል አድርጌ በሰላም ከተመለስኩ በዚህ ቦታ ላይ የልደታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያንን እሠራለሁ” ሲሉ ስዕለት ተስለው ወታደሮቻቸውን እየመሩ ወደ ጦርነቱ ዘመቱ፡፡ በጦርነቱም ከፍተኛ ተጋድሎ በማድረግ ድል አድርገው ተመለሱ፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ባደረገችላቸው መልካም ነገር በመደሰት ቃላቸውን ጠብቀው የመካነ ስብሐት ልደታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያንን ሱባኤ ይዘውበት በነበረበት ቦታ ላይ በ1703 ዓ.ም. ተከሉ፡፡

ቤተ ክርስቲያኗ በንጉሥ ዐፄ ዮስጦስ ስትመሠረት የነገሥታት ትክል በመሆኗ ብዙ ሰው በአጥቢያዋ አልነበረም፡፡ የምትተዳደረውም ሪም በሚባል ሥርዓት ነበር፡፡ /የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች ከአለቃው ጀምሮ እስከ ዲያቆናትና ዐቃቢት ድረስ በተዋረድ እንደ አገልግሎታቸው ከቤተ ክርስቲያኗ ጉልት እየተከፈለ መሬት ይሰጣቸዋል፡፡ ይህ ለአገልጋዮቹ የሚሰጣቸው መሬት ሪም በመባል ይታወቃል፡፡ የቤተ ክርስቲያኗ አገልጋዮችም ከተሰጣቸው ሪም ላይ ከሚኖሩ ዜጎች ዓመታዊ ምርት /እህል ብቻ/ ሢሶውን ለመተዳደሪያቸው ይቀበላሉ፡፡/ በጊዜው ቤተ ክርስቲያኗን ለሚያገለግሉ ከ150 በላይ ለሆኑ ሊቃውንት ደምቢያ ከሚባል አገር እህል ይጫንላቸው ነበር፡፡

አድርሺኝ

ከጎንደር መካነ ስብሐት ልደታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያን መተከል ጋር በተያያዘ በጎንደር ከተማ ውስጥ የሚካሔድ አንድ ሥርዓት አለ፡፡ ይህም ሥርዓት አድርሺኝ በመባል ይጠራል፡፡ ሥርዓቱ የሚከናወነው በፍልሰታ ጾም ወቅት ነው፡፡

ስለ ሥርዓቱ አጀማመር አባቶች ሲናገሩ፣ ዐፄ ዮስጦስ ወደ ጦርነት ሲዘምቱ “ጦርነቱን በልደታ ለማርያም ምልጃ ተደግፌ አሸንፌ ከተመለስኩ በፍልሰታ ለማርያም ሱባኤ ማታ ማታ ካህናቱን፤ መኳንንቱንና ምእመናንን ሰብስቤ ግብዣ አደርጋለሁ” በማለት ብፅዐት ይገባሉ፡፡ እርሳቸውም ድል አድርገው ተመለሱ፤ በቃላቸውም መሠረት ግብዣ አደረጉ፡፡ ሕዝበ ክርስቲያኑም እርሳቸውን ተከትሎ በጾመ ፍልሰታ ወቅት ይህን ሥርዓት ይተገብሩት ጀመር፤ ስያሜውም “አድርሺኝ” ተባለ፡፡

አድርሺኝ በመላው ጎንደር እስከ ዛሬ ድረስ በየቤተ ክርስቲያኑና በየአካባቢው በፍልሰታ ጾም ወቅት ይከናወናል፡፡ ምእመናን ከቅዳሴ መልስ ሱባኤው እስኪያልቅ በመረጡት አንድ ቤት ውስጥ ተሰብስበው ቆሎና ጠላ ተዘጋጅቶ በእመቤታችን ስም ጽዋ ይጠጣሉ። በተለይ መነኮሳያት እናቶች በሚታደሙበት ጽዋ ላይ “ኦ! ማርያም” የሚለውን የተማጽኖ መዝሙር ይዘምራሉ። ይህ መዝሙር በሚዘመርበት ጊዜ እመቤታችን ፊት ለፊት ስለምትቆም በፍፁም ተመስጦና መንበርከክ ያከናውኑታል።

በዋነኛነት የመካነ ስብሐት ልደታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ትምህርት ቤት ይህንን የተቀደሰ ተግባር በማስተባበርና በማስፈጸም እንዲሁም ትውፊቱ እንደጠበቀ ለተተኪው ትውልድ እንዲተላለፍ በማድረግ እየሠራ ይገኛል፡፡

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምና ዐፄ ዮስጦስ

gonder ledeta 2 ዐፄ ዮስጦስ ለእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የነበራቸው ፍቅር እጅግ ጥልቅ ከመሆኑ የተነሣ በርካታ ታሪኮች እንዳሏቸው ይነገራል፡፡ ከእነዚህም ውስጥ የጥምቀትን በዓል ለማክበር ዐፄ ዮስጦስ ከካህናቱ፤ ከመኳንንቱና ከምእመናን ጋር በመሆን ታቦቱን አጅበው ቀሃ ዳር ወደሚገኘው ጥምቀተ ባሕር በመውረድ ላይ ሳሉ አንዲት ሴት ከታቦቱ አጠገብ ስትጓዝ ይመለከታሉ፡፡ “ከታቦቱ አጠገብ የምትጓዘውን ሴት ከሥፍራው አርቋት፤ ከታቦት አጠገብ እንዴት ብትዳፈር ነው የምትጓዘው?” በማለት ለወታደሮቻቸው ትእዛዝ ያስተላልፋሉ፡፡ ወታደሮቻቸው ግን ንጉሡ ያሏትን ሴት ማግኘት አልቻሉም፡፡ እሳቸውም ሠይፋቸውን መዝዘው ቢሔዱም ከታቦቱ አጠገብ ተሰወረችባቸው፡፡

“ይህ ምሥጢር ሳይገለጽልኝ ወደ ንግሥናዬና ወደ ቤተ መንግሥቴ አልመለስም” በማለት እዚያው ድንኳን አስተክለው ሱባኤ ይገባሉ፡፡ በሦስተኛው ቀን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተገልጻ “ከታቦቱ አጠገብ ያየኸኝ እኔ ድንግል ማርያም ነኝ” በማለት ተናገረቻቸው፡፡ ጊዜ እረፍታቸውንም መች እንደሚሆን አስታውቃና ባርካ፤ በየዓመቱ ኅዳር 21 በአክሱም ጽዮን ማርያም፤ ለአስተርእዮ ማኅደረ ማርያም እንደምገኝ ሁሉ በጥምቀት በጎንደር መካነ ስብሐት ልደታ ለማርያም እገኛለሁ በማለት ቃል ኪዳን ገብታላቸዋለች፡፡

ምእመናን በቤተ ክርስቲያኗ የጥምቀት ዕለት ገንዘብ አዋጥተው ዝክር መዘከር የጀመሩት ከዚህ ቃል ኪዳን ጋር በተገናኘ መሆኑን አረጋውያን ያስረዳሉ።

ለውኃ ለውኃ ምን አለኝ ቀሃ

የቀሃ ወንዝ በጎንደር ውስጥ የጎንደርን ከተማ ለሁለት ከፍሎ ይልፋል፡፡ ቀሃ በጎንደር ውስጥ ታዋቂ ከመሆኑ የተነሣም “ለውኃ ለውኃ ምን አለኝ ቀሃ” እየተባለም ይነገራል፡፡ የጥምቀት በዓል በሚከበርበት ወቅት የልደታ ለማርያም ታቦት በዚሁ አካባቢ ታርፋለች፡፡

gonder ledeta 3 አረጋዊ መንፈሳዊ ስለ እንጦንስ የትውልድ አካባቢ ሲናገር ቀሃ ወንዝን እንደምልክትነት ይጠቀመዋል፡፡ ወንዝ ዳር፤ ወንዝ አካባቢ እንደሆነ ይነግረንና ምን ትመስላለች የሚለውን ሲገልጽ “ቀሃ ዳር ልደታ ማርያም እንዳለች ሁሉ . . . ” እያለ ያብራራል፡፡
የልደታ ውኃበጎንደር ከተማው ውስጥ በዛ ያሉ የጸበል ቦታዎች የሚገኙ ሲሆን ከእነዚህ የጸበል ቦታዎች አንዱ በመካነ ስብሐት ልደታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያን ይገኛል፡፡ የጸበል ቦታውም የልደታ ውኃ በመባል እየተባለ ይጠራል፡፡ በጸበሉ በርካታ ድውያን የሚፈወሱበት ሲሆን እንደ ግሸ አባይ ከምእራብ ወደ ምሥራቅ ይፈሳል፡፡

የልደታ ውኃ በተለያዩ የትርጓሜ መጻሕፍት ውስጥ ትገኛለች፡፡ መምህር ኤስድሮስ ውዳሴ ማርያምን ሲተረጉሙ “ዳዊት ዘነግሠ ለእሥራኤል አመ ይትነሥኡ ላዕሌሁ ዕልዋን ፈተወ ይስተይ ማየ እም ዓዘቅተ ቤተልሔም. . .፤ የሕይወት ውኃነት እንዳላት ከምእራብ ወደ ምሥራቅ እንደምትፈሰው እንደ ልደታ ውኃ” ይላል፡፡

በጸበሏ ዛሬም ድረስ በርካታ ሕሙማን እየተፈወሱ ይገኛሉ፡፡

ይቆየን

ማቴዎስ ወንጌል

 ሐምሌ 9 ቀን 2006 ዓ.ም.

ምዕራፍ አምስት

የተራራው ስብከት /አንቀጸ ብፁዓን/

ይህ ምዕራፍ ልዑለ ባሕርይ አምላክ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ተራራ ወጥቶ ከፍ ካለ ቦታ ተቀምጦ ያስተማረው ትምህርት በመሆኑ የተራራው ስብከት በመባል ይታወቃል፡፡ ብፁዓን እያለ በማስተማሩም አንቀጸ ብፁዓን ይባላል፡፡ ጌታችን ከፍ ካለ ቦታ ተቀምጦ ያስተማረበት ምክንያት፣ መምህር ከፍ ካለ ቦታ ተማሪዎች ደግሞ ዝቅ ካለ ቦታ ተቀምጠው የሚማሩት ትምህርት ስለሚገባ ነው፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ትምህርቱ አንቀጸ ብፁዓንን እንደሚከተለው አስተምሯል፡፡

  1. “በመንፈስ ድሆች የሆኑ ብፁዓን ናቸው፣ መንግሥተ ሰማያት የእነርሱ ናትና፡፡” ሀብትና ዕውቀት፣ ሥልጣንና ጉልበት እያላቸው የማይታበዩና የማይኮሩ፣ ሁሉ የእግዚአብሔር ነው ብለው ለእግዚአብሔር አሳልፈው የሚሰጡ ሰዎች ብፁዓን ይባላሉ፡፡ በመንፈስ ድሆች የሆኑ የተባለውም ለዚህ ነው፡፡ ጌዴዎን ኀያል ሲሆን እግዚአብሔርም እስራኤልን እንዲያድን በመረጠው ጊዜ በመንፈስ ድሃ ሆኖ ተገኝቷል፡፡ “ጌታ ሆይ እስራኤልን በምን አድናለሁ? ወገኔ ከምናሤ ነገድ ከሁሉ ይልቅ የተጠቃ ነው፡፡ እኔ በአባቴ ቤት የሁሉ ታናሽ ነኝ፡፡” ሲል ነው ለተገለጠለት የእግዚአብሔር መልአክ የመለሰው፡፡ መሳ.6፡12-15፡፡ በእግዚአብሔር ኃይል በሦስት መቶ ሰው ብቻ ምድያማውያንን ድል ካደረገ በኋላ የእስራኤል ልጆች ተሰብስበው አንተ ልጅህም የልጅህም ደግሞ ግዙን ባሉት ጊዜ በመንፈስ ድሃ ሆኖ የተገኘው የጌድዮን መልስ “እኔ አልገዛችሁም፣ ልጄም አይገዛችሁም እግዚአብሔር ይገዛችኋል፡፡” የሚል ነበር፡፡ እንዲህም በማድረጉ እስከ እድሜው ፍጻሜ ድረስ ለአርባ ዘመናት ሰላምና በረከት ዘመንን አሳለፈ፡፡ መሳ.8፡22-28፡፡ አብርሃም በእግዚአብሔር ፊት ሞገስ ያገኘ የእግዚአብሔር ወዳጅ ሲሆን በመንፈስ ድሃ የሆነ ሰው በመሆኑ እኔ አፈርና አመድ ነኝ ብሏል፡፡ ዘፍ.18፡3፣ ዘፍ.18፡25፣ ያዕ.2፡23፡፡ ልበ አምላክ ዳዊት ሰባት ሀብታት ፍጹም ጸጋ የተሰጠው የእግዚአብሔር የልብ ሰው ሲሆን በሰውም ሆነ በእግዚአብሔር ፊት ራሱን ድሃ ያደረገ ሰው ነበር፡፡ ንጉሡ ሳኦል ልጁን ሊድርለት ባለ ጊዜ “ለንጉሥ አማች እሆን ዘንድ እኔ ማነኝ? ሰውነቴስ ምንድነው?” ሲል ለንጉሡ መልሶለታል፡፡1ኛ.ሳሙ.18፡18፡፡ በእግዚአብሔር ፊት ሲዘምርም “እኔ ግን ትል ነኝ ሰውም አይደለሁም፤ ማላገጫ በሕዝብም ዘንድ የተናቅሁ ነኝ” ብሏል፡፡ መዝ.21፡6፡፡

  2. “የሚያዝኑ ብፁዓን ናቸው፡፡ መጽናናትን ያገኛሉና፡፡” ኃጢአታቸውን እያሰቡ እንደ አዳም፣ እንደ ዳዊትና እንደ ቅዱስ ጴጥሮስ የባልንጀራቸውን ኃጢአት እያሰቡ ለንጉሥ ሳኦል እንዳለቀ ሰው እንደ ሳሙኤል /1ኛ ሳሙ.16፡1/ ሰማዕታትን አያሰቡ ለቅዱስ እስጢፋኖስ እንዳለቀሱት ደጋግ ሰዎች፣ መከራ መስቀልን እያሰበ ሰባ ዘመን እንዳለቀሰው እንደ ፍቁረ እግዚእ ዮሐንስ የሚያዝኑ ሰዎች ብፁዓን ይባላሉ፡፡

  3. የዋሆች ብፁዓን ናቸው ምድርን ይወርሳሉና፡፡” ቂም በቀል የማያውቁ፣ አንድም ሰውነታችንን መክረን አስተምረን ማኖር እንደምን ይቻለናል? ብለው በምክረ ካህን በፈቃደ ካህን የሚኖሩ፣ በሞኝነት ሳይሆን አውቀው ስለ እግዚአብሔር ብለው የሚተው ኃዳግያነ በቀል የሆኑ ሰዎች ብፁዓን ናቸው፡፡ ዳዊት እግዚአብሔር በእጁ የጣለለትን ጠላቱን ሳኦልን መግደል ሲችል እራርቶ የተወው በሞኝነት ሳይሆን በየዋህነት ነው፡፡ 1ኛ.ሳሙ.24፡1-22፡፡ ጸሎቱም “አቤቱ ዳዊትን ገርነቱንም ሁሉ አስብ፤” የሚል ነበር መዝ.131፡1፡፡ የዋሃን ይወርሷታል የተባለችው ምድር መንግሥተ ሰማያት ናት፡፡ ምድር መባሏም ምድር አልፋ እርሷ የምትተካ፣ በምድር በሚሰራ የጽድቅ ሥራ የምትወረስ፣ ምድራውያን ጻድቃንም የሚወርሷት ስለሆነች ነው፡፡ “አዲስ ሰማይንና አዲስ ምድርንም አየሁ፣ ፊተኛው ሰማይና ፊተኛየቱ ምድር አልፈዋልና” ራእ.21፡1፣ “ምድርና ሰማይም ከፊቱ ሸሹ ስፍራም አልተገኘላቸውም” ራእ.20፡11፣ “እነሆ አዲስ ሰማይና አዲስ ምድር እፈጥራለሁና፡፡ የቀደሙትም አይታሰቡም፡፡” ኢሳ.65፡17፣ “ስለዚያ ቀን ሰማያት ተቃጥለው ይቀልጣሉ የሰማይም ፍጥረት በትልቅ ትኩሳት ይፈታል፡፡ ነገር ግን ጽድቅ የሚኖርባትን አዲስ ሰማይና አዲስ ምድር እንደተስፋ ቃሉ እንጠብቃለን፡፡”

  4. “ስለጽድቅ የሚራቡና የሚጠሙ ብፁዓን ናቸው ይጠግባሉና፡፡” ስለጽድቅ ብለው ረኃቡንና ጥሙን ታግሰው፣ የእግዚአብሔር መንግሥት በመብል በመጠጥ አትወረስም፣ አንድም ቢፈጽማት የእግዚአብሔርን መንግሥት የምታሰጥ አትወረስም፣ አንድም ቢፈጽሟት የእግዚአብሔርን መንግሥት የምታሰጥ ወንጌል በመንፈስ ቅዱስ የሆነ እምነትን ተስፋንና ፍቅርን እንጂ መብል መጠጥን አትሰብክም አንድም ልብላ ልጠጣ በምትል ሰውነት ወንጌል አትዋሐድም /ሮሜ.14፡19/ መብል ግን ወደ እግዚአብሔር አያቀርበንም ባንበላ ምንም አይጐድልብንም ብንበላም ምንም አናተርፍም /1ኛ.ቆሮ.8፡8/፡፡ መብል ለሆድ ነው፣ ሆድም ለመብል ነው፤ እግዚአብሔር ግን ይህንም ያንም ያጠፋቸዋል፡፡ ብለው የሚጾሙ ሰዎች ብፁዓን ይባላሉ፡፡ “ጽድቅን የሚራቡና የሚጠሙ” ሲልም እውነት በሕይወታቸው ነግሣባቸው የሚኖሩትን ያመለክታል፡፡ ጾመ ሙሴ ዘዳ.9፡9፣ ጾመ አስቴር 4፡16፣ 9፡31 ጾመ ዳንኤል፣ ዳን.10፡2 ጾመ ዳዊት፣ 2ኛ ሳሙ.12፡22 መዝ.108፡24፣ ጾመ ሐዋርያት የሐዋ.13፡2 ወዘተ ተመልከት፡፡

  5. “የሚምሩ ብፁዓን ናቸው፡ ይማራሉና” የሚምሩ ሲል ምሕረት ሥጋዊ፣ ምሕረት መንፈሳዊና ምሕረት ነፍሳዊ የሚያደርጉትን ማለቱ ነው፡፡ ምሕረት ሥጋዊ ቀድዶ ማልበስ፣ ቆርሶ ማጉረስ፣ ቢበድሉ ማሩኝታ እና ቢበድሉ ይቅርታ ነው፡፡ ምሕረት መንፈሳዊ ክፉው ምግባር በጐ ምግባር መስሎት ይዞት የሚኖረውን ሰው መክሮ አስተምሮ ከክፋት ወደ በጐነት መመለስ ነው፡፡ ምሕረት ነፍሳዊ ደግሞ ክፉ ሃይማኖት በጐ ሃይማኖት መስሎት የሚኖረውን ሰው መክሮ አስተምሮ ወደ ቀናው ሃይማኖት መመለስ ነው፡፡

  6. “ልበ ንጹሖች ብፁዓን ናቸው፡፡ እግዚአብሔርን ያዩታልና፡፡” በንስሐ ከኃጢአት እንዲሁም ከቂምና ከበቀል ንጹሓን የሆኑ ከንጽሐ ልቡና የደረሱ ሰዎች ብፁዓን ይባላሉ፡፡ “ሁል ጊዜ እግዚአብሔርን በፊቴ አየዋለሁ፤ በቀኜ ነውና አልታወክም፡፡ ስለዚህ ልቤን ደስ አለው ምላሴም ሐሴት አደረገች፡፡ ሥጋዬ ደግሞ በተስፋ ታድራለች፡፡” መዝ.15፡8፡፡ እነቅዱስ እስጢፋኖስ ለነጽሮተ ሥሉስ ቅዱስ የደረሱት ልበ ንጹሐን በመሆናቸው ነው የሐዋ.7፡56፡፡

  7. “የሚያስተራርቁ ብፁዓን ናቸው የእግዚአብሔር ልጆች ይባላሉና፡፡” ሰውን ከሰው፣ ሰውን ከእግዚአብሔር የሚያስታርቁ ሰዎች ብፁዓን ይባላሉ፡፡ መልከጼዴቅ የተጣሉትን ሲያስታርቅ ይውል ነበር፡፡

  8. “ስለ ጽድቅ የሚሰደዱ ብፁዓን ናቸው መንግሥተ ሰማያት የእነርሱ ናትና፡፡” ለመማር፣ ለማስተማር፣ ለምናኔ እንዲሁም በሃይማኖት ምክንያት ሀገራቸውን ጥለው የሚሰደዱ ሰዎች ብፁዓን ይባላሉ፡፡ “ሁሉን እያጡ መከራን እየተቀበሉ፣ እየተጨነቁ የበግና የፍየል ሌጦ ለብሰው ዞሩ፡፡ ዓለም አልተገባቸውምና በምድረ በዳና በተራራ፣ በዋሻና በምድር ጉድጓድ ተቅበዘበዙ፡፡” ዕብ.11፡37፡፡ ብሎ ቅዱስ ጳውሎስ የተናገራቸው ስለ ጽድቅ ብለው የተሰደዱትን ነው፡፡ አብርሃም ከከለዳውያን ዑር ከሀገሩ ወጥቶ በባዕድ ሀገር ሲንከራተት የኖረው ተጠብቆ የሚቆየው ተስፋ ጸንቶ ነበር፡፡ የተስፋውም ባለቤት እግዚአብሔር የተስፋውን ዋጋ እንዲያገኝ አደረገው፡፡ ያዕ.2፡23፣ ዘፍ.15፡6፣ ኢሳ.41፡8፡፡

  9. “ሲነቅፏችሁና ሲያሳድዷችሁ በእኔ ምክንያት ክፉውን ሁሉ በውሸት ሲናገሩባችሁ ብፁዓን ናችሁ ዋጋችሁ በሰማያት ታላቅ ነውና ደስ ይበላችሁ፣ ሐሴትም አድርጉ፤ ከእናንተ በፊት የነበሩትን ነቢያትን እንዲህ አሳደዋቸዋልና፡፡” በመነቀፍ፣ በመሰደድ፣ በአሉባልታ የሚፈተኑትን ፈተና በትዕግስት ማሸነፍ እና ስለ እውነት መከራን መቀበል የማያልፍና የማይለወጥ ፈጹም ሀብትን ከእግዚአብሔር ዘንድ ያሰጣል፡፡ ለዚህም ነው ጌታችን ዋጋችሁ በሰማያት ታላቅ ነውና ደስ ይበላችሁ፡፡” ሲል ያስተማረው፡፡

ክርስቲያን የምድር ጨው ሆኖ በምግባሩ አልጫ ሕይወት ያላቸውን ሰዎች ሕይወት ማጣፈጥ እንደሚገባውም ያስተማረው በዚሁ ክፍል ነው፡፡ ነገር ግን ጨውነቱን ትቶ አልጫ ሆኖ ቢገኝ እንኳን ሌላውን ሊያጣፍጥ ለራሱም ወደውጭ ተወርውሮ እንደሚረገጥ ከመንግሥተ ሰማያት በአፍአ እንደሚቀር ለምንም እንደማይጠቅም አስገንዝቧል፡፡

 

በመቀጠልም እናንተ የዓለም ብርሃን ናችሁ፡፡ በተራራ ላይ ያለች ከተማ እንዳትሰወር ተራራው ይገልጣታል፡፡ መብራትን ከእንቅብ በታች ሣይሆን በቤቱ ላሉ ሁሉ እንዲያበራ በመቅረዝ ያኖሩታል፡፡ መቅርዙም ከፍታ ፋናውን ይገልጸዋል ሲል ተናግሯል፡፡

 

ፍሬ ነገሩም ያለው በተራራ ላይ ያለች ከተማ እና በመቅረዝ ላይ ያለ መብራት አይሰወሩም፤ የተራራውና የመቅረዙ ከፍታ ይገልጣቸዋል የሚለው ላይ ነው፡፡ ምሥጢሩም፡-

  • እናንተ ሥራውን አብዝታችሁ ሥሩ ግድ በተአምራት ይገልጻችኋል፣

  • ከሥጋ ጋር የተዋሐደች ነፍስ ሥራ ሠርታ ልትገለጽ ነው እንጂ ተሰውራ ልትቀር አይደለም፣

  • ከሥጋ ጋር የተዋሐደ መለኮት አስተምሮ ተአምራት አድርጐ አምላክነቱን ሊገልጽ ነው እንጂ ተሰውሮ ሊቀር አይደለም፡፡

  • የተሰቀለ ጌታ ሞቶ ተነሥቶ አምላክነቱን ሊገልጽ ነው እንጂ ሞቶ ሊቀር አይደለም፡፡

  • ወንጌል በአደባባይ ተገልጻ ልትነገር ነው እንጂ ተሰውራ በልባችሁ ልትቀር አይደለም፡፡ ማለት ነው፡፡ “መልካሙን ሥራችሁን አይተው በሰማያት ያለውን አባታችሁን እንዲያከብሩ ብርሃናችሁ እንዲሁ በሰው ፊት ይብራ፡፡” በማለትም እግዚአብሔር የሚከበርበትንና የሚመሰገንበትን ሥራ እንዲሠሩ ተናግሯል፡፡

 “ሕግንና ነቢያትን ለመሻር ነው የመጣው” የሚለውን የአይሁድ አሉባልታ ለማጥፋት ሕገ ኦሪትንና ትንቢተ ነቢያትን ለመሻር ሳይሆን ለመፈጸም የመጣ መሆኑን ያስረዳውም በዚሁ ክፍል ነው፡፡ ሰማይና ምድር እስኪያልፍ ድረስ ከሕግ አንዲት የውጣ አንዲት ነጥብ እንደማታልፍ አረጋግጧል፡፡ አትግደልን በአትቆጣ /ማቴ.5፡22/፣ አታመንዝርን “ወደሴት ያየ ሁሉ የተመኛትም ያን ጊዜ በልቡ አመንዝሯል” /ማቴ.5፡28/ በሚለው ላጸናቸው መጥቻለሁ ማለቱ ነው፡፡ ከዚህ የወጣ ግን ከመንግሥተ ሰማያት በአፍአ እንደሚቀር አስገንዝቧል፡፡ ይህም ሕገ ኦሪትን ሽሯል ለሚሉ ለዘመናችንም ተረፈ አይሁድ ታላቅ መልስ ነው፡፡ ስለመሰናክል ሲያስተምርም ዓይንህ ብታሰናክልህ አውልቀህ ጣላት፡፡ እጅና እግርህም ቢያሰናክሉህ ቆርጠህ ጣላቸው ብሏል፡፡ 

 

ዓይን የተባለች ሚስት ናት እጅ የተባለ ልጆች፣ እግር የተባሉ ቤተሰቦች ናቸው፡፡ ምሥጢሩም ሚስትህ ያልሆነ ሥራ ላሰራህ ብትለህ ፈቃዷን አፍርስባት፡፡ ዛሬ በዚህ ዓለም የሚስትህን ፈቃድ ፈጽመህ ኖረህ ኋላ ገሃነም ከምትገባ በዚህ ዓለም የሚስትህን ፈቃድ አፍርሰህ ኖረህ ኋላ መንግሥተ ሰማያት ብትገባ ይሻልሃልና፡፡ ወድቀው ይነሱ በእጅ ዘግይተው ይከብሩ በልጅ እንዲሉ ልጆችህ ያልሆነ ሥራ እናሰራህ ቢሉ ፈቃዳቸውን አፍርስባቸው፡፡ በዚህ ዓለም የልጆችህን ፈቃድ ፈጽመህ ኖረህ ኋላ ገሃነም ከምትወርድ በዚህ ዓለም የልጆችህን ፈቃድ አፍርሰህ ኖረህ ኋላ መንግሥተ ሰማያት ብትገባ ይሻልሃልና፡፡ እግር የተባሉ ቤተሰቦችህ ምክንያተ ስሕተት ሆነው ያልሆነ ሥራ እናሠራህ ቢሉህ ፈቃዳቸውን አፍርስባቸው፤ በዚህ ዓለም የእነሱን ፈቃድ ፈጽመህ ኖረህ ኋላ ገሃነም ከምትገባ ፈቃዳቸውን አፍርሰህ ኖረህ ኋላ መንግሥተ ሰማያት ብትገባ ይሻልሃልና አንድም እንደ ዓይንህ፣ እንደ እጅህ እና እንደ እግርህ ማለትም እንደራስህ የምትወደው ባልንጀራህ ያልሆነ ሥራ አሠራሃለሁ ቢልህ ፈቃዱን አፍርስበት ማለት ነው፡፡

 

በመጨረሻም ዓይን ያጠፋ ዓይኑ ይጥፋ፤ ጥርስ የሰበረም ጥርስ ይሰበር የሚለው፣ ጠላትህ ቢራብ አብላው ቢጠማም አጠጣው” በሚል ሕገ ትሩፋት ወንጀል መተካት እንደሚገባውና በቀልም የክርስቲያኖች ገንዘብ አለመሆኑን አስተምሯል፡፡

  • ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 4ኛ ዓመት ቁጥር 2 ኅዳር 1989 ዓ.ም.