Emebetachin-Eriget

“ወልድኪ ይጼውአኪ ውስተ ሕይወተ ወመንግሥተ ክብር” ልጅሽ ወደ ሕይወትና ክብር መንግሥት ይጠራሻል፡፡

ነሐሴ 15 ቀን 2004 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ
 

እንኳን ለወላዲተ አምላክ ለቅድስት ድንግል ማርያም የትንሣኤ በዓል በሰላም አደረሳችሁ እያልን ፈጣሪያችን በዓሉን የበረከት፣ የረድኤት ያድርግልን፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በየዓመቱ ነሐሴ 16 ቀን የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያምን ትንሣኤ በታላቅ መንፈሳዊ ሥነ ሥርዓት ታከብራለች፡፡

ቅዱስ ያሬድ የእመቤታችንን ፍልሰተ ሥጋ አስመልክቶ ዝማሬ በተባለው ድርሰቱ “በስብሐት ውስተ ሰማያት መላእክት ወሊቃነ መላእክት ወረዱ ለተቀብሎታ፣ እብለኪ ወእሙ ለእግዚእየ እብለኪ ዳዊት አቡሃ ምስለ መሰንቆሁ ሙሴኒ እንዘ ይፀውር ኤፉደ መጽኡ ሃቤሃ ጴጥሮስ ወጳውሎስ ሐዋርያት አጠኑ ሥጋሃ በማዕጠንተ ወርቅ፣ ሱራፌል ወኪሩቤል ሰፍሑ ከነፊሆሙ ላዕሌሃ፣ ወረደ ብርሃን እምሰማያት ወመብረቀ ስብሐት እምውስተ ደመናት፣ ተለዓለት እምድር ውስተ አርያም በስብሐት ወበህየ ነበረት ዘምስለ ወልዳ በየማነ አብ ወመንፈስ ቅዱስ” ብሏል፡፡ ይኸውም “መላእክትና ሊቃነ መላእክት ቅዱስ ሥጋዋን ለማሳረግ በታላቅ ምሥጋና ከሰማይ ወረዱ፤ አባቷ ዳዊት ከመሰንቆው ጋር ሙሴም የአገልግሎት ልብሱን ለብሶ፣ ሐዋርያት ጴጥሮስና ጳውሎስም ወደ እርሷ መጡ ሥጋዋንም በወርቅ ማዕጠንት አጠኑ፡፡ ሱራፌልና ኪሩቤልም በላይዋ ክንፎቻቸውን ዘረጉ /ጋረዱ/፡፡ ከሰማያት ብርሃን የምስጋና መብረቅም ከደመናት ውስጥ ወጣ፡፡ ከምድር ወደ ሰማያት በምስጋና ከፍ ከፍ አለች ከልጇ ጋርም በአብና በመንፈስ ቅዱስ ቀኝ ተቀመጠች” ማለት ነው፡፡ ይህም “በወርቅ ልብስ ተጎናጽፋና ተሸፋፍና ንግሥቲቱ በቀኝህ ትቆማለች፡፡” መዝ.44፥9 ተብሎ የተነገረላትን ቃለ ትንቢት የተፈጸመላት መሆኑን ያመለክታል፡፡

 

የዚህም ጥንተ ነገሩ እንደምን ነው ቢሉ ታሪኩ ይህን ይመስላል፡-

እሑድ ጥር 21 ቀን እመቤታችን አርፋለች፡፡ ሐዋርያት ባጎበር አድርገው ወደ ጌቴ ሴማኒ ይዘዋት ሲሄዱ አይሁድ “ቀድሞ ልጇን ሰቅለን ብንገድለው ደቀ መዛሙርቱ ተነሣ፣ ዐረገ” እያሉ ሲያውኩን ኖሩ፤ ዛሬ ደግሞ እርሷን ተነሣች፣ ዐረገች እያሉ ሊያውኩን አይደለምን? በእሳት እናቃጥላታለን” ብለው ተነሡ፡፡ ታውፋንያ የሚባል አይሁዳዊ ተራምዶ አጎበሩን ጨበጠው፡፡ መልአኩ ቅዱስ ሩፋኤል የታውፋንያን ሁለት እጁን በሰይፍ መትቶ ቀጣው፡፡ በዚህም የታውፋንያ ሁለት እጁ ከአጎበሩ ተንጠልጥሎ ቀረ፡፡ ከዚያ በኋላ መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌላዊውን ቅዱስ ዮሐንስ ጨምሮ በደመና ነጥቆ ከገነት በዕፀ ሕይወት ሥር አኖራት፡፡ ሐዋርያት ዮሐንስን “እንደምን ሆነች” አሉት፡፡ እርሱም፡- “በገነት ከዕፀ ሕይወት ሥር አለች” አላቸው፡፡ “ዮሐንስ አይቶ እኛ ሳናይ” ብለው፤ በነሐሴ መባቻ ጾም ጀመሩ፤ ሰኞ ነሐሴ 1 ቀን ጀምረው እሑድ ነሐሴ 14 ቀን ፈጽመዋል፡፡ በዚሁ ቀን ጌታችን ትኩስ በድን አድርጎ የእመቤታችንን ሥጋ ሰጥቷቸው ቀብረዋታል፡፡ እርሷም እንደ ልጇ በተቀበረች በሦስተኛው ቀን /ማክሰኞ/ ተነሥታ አርጋለች፡፡ “ከመ ትንሣኤ ወልዳ” ያሰኘውም ይህ ነው፡፡ በዚሁ ጊዜ ከሐዋርያት ወገን የሆነው ቅዱስ ቶማስ አልነበረም፡፡ ደመና ጠቅሶ ከሀገረ ስብከቱ /ከሕንድ/ ሲመጣ ስታርግ አገኛት፡፡ “ወፈቀደ ይደቅ እምደመናሁ” ይላል፤ ተበሳጨ፡፡ “ቀድሞ የልጅሽን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁ፤ ዛሬ ደግሞ ያንቺን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁኝ” አለ፡፡ በዚህ ጊዜ የልቡናን ሐዘን የምታቀል እመቤታችን፡- አይዞህ አትዘን እኒያ ትንሣኤዬን ዕርገቴን አላዩም፡፡ አንተ አይተሃል፡፡ ተነሣች፣ ዐረገች ብለህ ንገራቸው፡፡” ብላEmebetachin-Eriget የያዘችውን ሰበን ሰጥታ ሰደደችው፡፡ ከዚህ በኋላ ሄዶ፤ “የእመቤታችን ነገር እንደምን ሆነ?” አላቸው “ሥጋዋን አግኝተን ቀበርናት” አሉት፡፡ እርሱም “ሞት በጥር በነሐሴ መቃብር ተዉ ይህ ነገር አይመስለኝም” አላቸው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ “አንተ እንጂ ልማድህ ነው፡፡ አንተ ብቻ ተጠራጥረህ አትቀርም፤ አንተ እየተጠራጠርህ ሰውን ሁሉ ስታጠራጥር ትኖራለህ” አለው፡፡ እርሱም የያዘውን ያውቃልና ጸጥ ብሎ ይሰማቸዋል፡፡ ከዚህ በኋላ ቅዱስ ጴጥሮስ ተቆጥቶ ሂዶ መቃብሩን ቢከፍተው የእመቤታችን ሥጋዋን አጥቷል፡፡ በዚህም ምክንያት ደንግጦ ቆመ፡፡ ይህን ጊዜ ቅዱስ ቶማስ “አታምኑኝም ብዬ ነው እንጂ እመቤታችንስ ተነሣች ዐረገች” አላቸው፡፡ የያዘውንም ሰበን እያሳያቸው፡- “ቅዱስ ሥጋዋን የገነዛችሁበት ጨርቅ /ሰበን/ ይህ አይደለምን” ብሎ ሰበኑን ሰጣቸው፡፡ ይህንንም ለበረከት ተካፍለውታል፡፡ ከዚህ በኋላ በዓመቱ “ቶማስ ትንሣኤሽን ዕርገትሽን አይቶ እኛ ሳናይ በማለት ጾም ጀመሩ፡፡ በ16ኛው ቀን እመቤታችንን መንበር ቅዱስ ጴጥሮስን ንፍቅ ቄስ፣ እስጢፋኖስን ሠራዒ ዲያቆን አድርጎ ራሱ ቀድሶ አቁርቦአቸዋል፡፡

 

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በእናት አባቷ ቤት 3 ዓመት፣ በቤተ መቅደስ 12 ዓመት፣ ጌታችንን ከወለደችበት ጊዜ አንሥቶ ለ33 ዓመት ከ3 ወር ከተወዳጅ ልጇ ጋር፣ ለ15 ዓመት ከ9 ወር ከቅዱስ ዮሐንስ ጋር፣ በአጠቃላይ በዚህች ምድር ለ64 ዓመታት ቆይታ በተነገረላት ተስፋ ትንሣኤና ትንቢት መሠረት እርሷም እንደ ልጇ ወደ መቃብር በወረደች በሦስተኛው ቀን በልጇ ፈቃድ ከሙታን ተለይታ ተነሥታለች፡፡

 

“አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ፥ አንተና የመቅደስ ታቦት” /መዝ.131፥8/ የሚለው የነቢየ እግዚአብሔር የቅዱስ ዳዊት ቃልም ፈጻሜውን አግኝቷል፡፡

እግዚአብሔር አምላካችን ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም በረከት ረድኤት ያሳትፈን፡፡

abune paulos

“የኢትዮጵያ መምህሯ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡”

ብፁዕ ወቅዱስ ዶ/ር አቡነ ጳውሎስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ፣ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳሳ ዘአክሱም፣ ወእጨጌ ዘመንበረabune paulos ተክለ ሃይማኖት የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ፕሬዚዳንት ለ ሐመር መጽሔት ዝግጅት ክፍል በ1991 ዓ.ም ስለ

  • ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስ አገልግሎት
  • ንዋያተ ቅዱሳት አጠባበቅ
  • ዘመናዊ የቤተ ክርስቲያን የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት
  • ገጠሪቱ ቤተክርስቲያ (አብነት ት/ቤቶችና ገዳማት )
  • ቤተክርስቲያን ለጥቁር አፍሪካውያን ለመድረስ ያላትን ዝግጁነትና አለማቅፋዊ አገልግሎት
  • የወጣቶች አገልግሎትና የሰንበት ት/ቤት መርሐግብር
  • የግል ሕይወታቸውና ሌሎች ጉዳዮች ላይ የሰጡትን ቃለ ምልልስ እንደሚከተለው አስተናግደነዋል። እዚህ በመጫን ያንብቡ
synodos akabi meneber

የዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክ ምርጫ አስመልክቶ የቅዱስ ሲኖደስ ጽ/ቤት መግለጫ ሰጠ፡፡

ነሐሴ 14 ቀን 2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

{gallery count=1 width=350 height=300 counter=1 links=0 alignment=center animation=3000}synodos{/gallery}

ብፁዕ ወቅዱስ ዶ/ር አቡነ ጳውሎስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ፣ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳሳ ዘአክሱም፣ ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ፕሬዚዳንት ነሐሴ 10 ቀን 2004 ዓ.ም. ከዚህ ዓለም በሞተ ሥጋ በመለየታቸው ቅዱስ ሲኖዶስ በዛሬው ዕለት ነሐሴ 14 ቀን 2004 ዓ.ም. ባደረገው ስብሰባ ዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክ መረጠ፡፡

 

መግለጫውን የሰጡት ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል የከፋ ሸካ ቤንችና ማጂ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሓፊ ሲሆኑ “በሕገ ቤተ ክርስቲያኑ አንቀጽ 17 መሠረት ቀደምትነት ካላቸው ብፁዓን አባቶች መካከል በመምረጥ ዋናው የፓትርያርክ ምርጫ እስከሚከናወን ድረስ ብፁዕ አቡነ ናትኤል የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፥ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክ ሆነው እየሠሩ እንዲቆዩ በቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ተወስኗል” በማለት ገልጸዋል፡፡

 

“የቤተ ክርስቲያኒቱ መንፈሳዊም ሆነ ማኅበራዊ ተግባር ዘርፈ ብዙ በመሆኑ ይህንኑ ከፍጻሜ ለማድረስ ቋሚ ሲኖዶሱን ማጠናከር አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቷል” ያሉት ብፁዕነታቸው የዋናው ፓትርያርክ ምርጫ እስከ ሚከናወን ድረስ ከዐቃቤ መንበረ ፓትርያርኩና ከቋሚ ሲኖዶስ ጋር አብረው የሚሠሩ ሰባት አባላት መመረጣቸውን ጨምረው ገልጸዋል፡፡

 

በዚህም መሠረት፡-

  1. ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ሓላፊ

  2. ብፁዕ አቡነ ገብርኤል የሲዳማና ጌዴዎ አማሮ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ

  3. ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ የጅማ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ

  4. ብፁዕ አቡነ ሉቃስ በክልል ትግራይ የምዕራብ ሴቲት ሁመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ

  5. ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል የልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን ሊቀ ጳጳስ

  6. ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ የወላይታና ዳውሮ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ

  7. ብፁዕ አቡነ አብርሃም የምሥራቅ ሀረርጌና የኦጋዴን አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ሆነው ተመርጠዋል፡፡

ሰሞኑን የዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክ ምርጫ ከቅዱስ ፓትርያርኩ ሥርዓተ ቀብር በኋላ እንደሚሆን የተገለጸ ቢሆንም ቅዱስ ሲኖዶስ ባደረገው ውይይት ዐቃቤ መንበር መምረጡ አስፈላጊ ሆኖ መገኘቱ በመግለጫው ተወስቷል፡፡ እንደ ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል ገለጻ  “መንበሩ ያለ ሓላፊ መቆየት የሌለበት በመሆኑና ከሀገር ውስጥም ሆነ ከውጭ የሚመጡ እንግዶችን ተቀብሎ የሚያሰናብት አባት መኖር አስፈላጊ ስለሆነ ቅድሚያ ተሰጥቶታል፡፡”

 

synodos akabi meneber

picture2

01 abune natenale

ሰበር ዜና ቅዱስ ሲኖዶስ አቃቤ መንበር ሰየመ

ነሐሴ 14 ቀን 2004 ዓ.ም.

 

በእንዳለ ደምስስ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ01 abune natenale ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በዛሬው ዕለት ባደረገው አስቸኳይ ስብሰባ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን የሚመራ ዐቃቤ መንበር ሰየመ፡፡ በዚህም መሠረት ብፁዕ አቡነ ናትናኤል የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ዐቃቤ መንበር ሆነው የተሾሙ ሲሆን ቅዱስ ሲኖዶስ ፓትርያርክ እስኪመርጥ ድረስ ቤተ ክርስቲያንን በበላይነት ይመራሉ፡፡

mkresearcher

የ፬ኛ ዓመታዊ ዐውደ ጥናት ግብዣ

mkresearcher

Debre_Tabor

ደብረ ታቦር

ሐሴ 13 ቀን 2004 ዓ.ም.

በመ/ር ምሥጢረ ሥላሴ ማናየ

“ወኮነት ደብረ ታቦር አምሳለ ቤተ ክርስቲያን እስመ አስተጋብአት እም ብሉይ ወሐዲስ”

 

ደብረ ታቦር የቤተ ክርስቲያን ምሳሌ ነች፤ ከብሉይና ከሐዲስ ሰብስባለችና፡፡ ከብሉይ ኪዳን ነቢያት ሙሴና ኤልያስን ከሐዲስ ኪዳን ሐዋርያት ጴጥሮስን ያዕቆብን፣ ዮሐንስን ከመምህራቸው ከክርስቶስ ጋር ሰብስባለችና፡፡ ቤተ ክርስቲያን በነቢያትና በሐዋርያት መሠረትነት ላይ ተመሥርታለች “እስመ ተሐነጽክሙ ዲበ መሠረተ ነቢያት ወሐዋርያት እንዘ ክርስቶስ ርዕሰ ማዕዘንተ ሕንጻ”  “በነቢያትና በሐዋርያት መሠረት ላይ ታንጻችኋል፤ የማዕዘኑም ራስ ደንጋይ ክርስቶስ ነው” እንዲል፡፡ኤፌ. 2፥20

የታቦር ተራራ

፩. የቤተ ክርስቲያን

፪. የወንጌል

፫. የመንግሥተ ሰማያት ምሳሌ ነው፡፡

 

አንደኛውን ምሳሌ ከላይ የተመለከትን ሲሆን ሁለተኛው ምሳሌ አበው መተርጉማን በትርጓሜአቸው እንዲህ አብራርተውታል፡፡ ተራራ ሲወጡት አድካሚ ነው ከወጡት በኋላ ግን ሁሉንም ቁልጭ አድርጎ ሲያሳይ ደስ ያሰኛል፤ ወንጌልም ሲማሯት፤ ሲያስተምሯት ታደክማለች፤ ከተማሯት በኋላ ግን ጽድቅና ኀጢአትን ፤እውነትንና ሐሰትን ለይታ ስታሳውቅ ደስ ታሰኛለችና”፡፡ “በሌላ መልኩ ከተራራ ላይ ያለ ሰው ጠላቱን በቀላሉ በአፈር በጠጠር ድል መንሣት፣ ፍትወታት እኩያትን ማሸነፍ ይችላል፡፡ ከተራራ ላይ ያለ ልሰወር ቢል እንዳይችል በወንጌል ያመነ ሰውም ተሰውሮ አይቀርም በመልካም ሥራው ለሁሉም ይገለጣል፡፡ በሦስተኛውም ተራራው የመንግሥተ ሰማያት ምሳሌ ነው፡፡ ከነቢያት ሁለቱ ከሐዋርያት ሦስቱ በተራራው ላይ መገኘታቸው መንግሥተ ሰማያት ነቢያትም ሐዋርያትም አንድ ሆነው የሚወርሷት መሆኑን ያስረዳል፡፡ ከደናግ ኤልያስዮሐንስ ከመአስባን (በሕግ ጋብቻ ኖረው ሚስቶቻቸው የሞቱባቸው ወይም ትዳራቸውን የተው) ሙሴ ጴጥሮስ በተራራው ላይ መገኘታቸውም መንግሥተ ሰማያት ደናግም መአስባንም መልካም ሥራ ሠርተው በአንድነት የሚወርሷት እንደሆነ ይገልጻል፡፡

እንዲሁም ተራራ ሲወጡት አድካሚ ነው መንግሥተ ሰማያት በብዙ ድካም ትወረሳለችና “እስመ በብዙህ ጻማ ሐለወነ ንበአ ውስተ መንግሥተ እግዚአብሔር” ወደ እግዚአብሔር መንግሥት በብዙ መከራ እንገባ ዘንድ አለን” እንዲል ሐዋ.14፥23 ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ብርሃነ መለኮቱን በደብረ ታቦር የገለጸበት ምክንያት ምሥጢር በብዙ ድካም እንጂ ምንም ሳይደክሙ እንደማይገኝ ሲገልጽ ነው፡፡ ለደቀ መዛሙርቱ ብዙዎቹን ምሥጢራት የገለጠላቸው ከከተማ ውጭ ነው፡፡ ቀደም ሲልም ለሙሴ የቃል ኪዳኑን ጽላት ሲሰጠው ወደ ሲና ተራራ በመጥራት ነበር፡፡ ነገረ ሥጋዌውንም በነበልባልና በእሳት አምሳል የገለጠለት በኮሬብ ተራራ በጎቹን አሰማርቶ በነበረበት ጊዜ እንደሆነ መጻሕፍት ይመሰክራሉ ዘፀ.3፥1 ምሥጢር ይገለጽልን ባላችሁ ጊዜ ወደ ቤተ ክርስቲያን ገስግሱ ቤተ ክርስቲያንን ደጅ ጽኑ ለማለት ነው፡፡ ወደ ተራራውም ሲወጣ ስምንቱን ደቀ መዛሙርቱን ከይሁዳ ጋር ከተራራ እግር ስር ትቶ ሦስቱን አስከትሎ ወጥቷል፡፡ ለሦስቱ በተራራው ላይ የተገለጠው ድንቅ ምሥጢርም ከእግረ ደብር ላሉት በሳምንቱ ተገልጿል፤ ከይሁዳ በቀር፡፡ ለዚህ ምሥጢር ብቁ ያልነበረው ይሁዳ ብቻ ነው፡፡ ይህም የሚያስተምረን ተገቢውን ምሥጢር ለተገቢው ሰው መንገር እና ለማይገባው ከመንገር መቆጠብ ተገቢ መሆኑን ነው፡፡ “እመኒ ክዱን ትምዓርትነ ክዱን ውእቱ ለህርቱማን ወለንፉቃን” ወንጌላችን የተሰወረ ቢሆንም እንኳን ፥ የተሰወረባቸው ለሚጠፉት ነው፡፡ እግዚአብሔርን የሚመስለው የክርስቶስ የክብሩ ወንጌል ብርሃን እንዳያበራላቸው የዚህ ዓለም አምላክ ልባቸውን አሳውሯልና፡፡ 2ቆሮ.4፥3-5 ያለው የሐዋርያው ትምህርት ይህን መሰል ምሥጢር ለሚገባው እንጂ ለማይገባው መግለጽ ተገቢ አለመሆኑን ነው፡፡

 

በዓለ ደብረ ታቦር

እንደሚታወቀው በቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዘጠኙ ዐበይት /ታላላቅ/ በዓላት አንዱ በዓለ ደብረ ታቦር ነው፡፡ ከዐበይት በዓላት የተመደበበትም ምክንያት በደብረ ታቦር የተገለጸው ምሥጢር ድንቅ በመሆኑ ነው፡፡ ክብር ምስጋና ይግባውና ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለደቀ መዛሙርቱ አንድ አንድ ጊዜ ለሁሉም፤ አንድ አንድ ጊዜ ደግሞ በከፊል ምሥጢራትን ገልጾላቸዋል፡፡ ከእነዚህም ምሥጢራት የሚከተሉት ተጠቃሾች ናቸው ምሥጢረ ትንሣኤ ሙታንን በቤተ አልዓዛርና በቤተ ኢያኤሮስ፣ ምሥጢረ ቊርባንን እንዲሁ በአልዓዛር ቤት፣ ነገረ ምጽአትን በደብረ ዘይት ገልጿል፡፡ ማቴ.9፥23፣ 26፥26፣24፥3፣ ዮሐ.11፥43 ከእነዚህ ከላይ ከተዘረዘሩት ምሥጢራት ምሥጢረ ትንሣኤ ሙታንና ምሥጢረ ቊርባንን ሁሉም ደቀ መዛሙርት ያዩ ሲሆን ነገረ ምጽአትን ግን በከፊል ከደቀ መዛሙርቱ ጴጥሮስ፣ ያዕቆብና ዮሐንስ አራተኛ እንድርያስን ጨምረው ተረድተዋል፡፡ ደብረ ታቦርን ከዚህ ልዩ የሚያደርገው ከሐዋርያት ጴጥሮስ፣ ዮሐንስና ያዕቆብ ያሉ ሲሆን ከነቢያት ሙሴና ኤልያስ መጨመራቸው ነው፡፡ ከጌታችን ዘጠኝ በዓላት አንድ አንዶቹ በተፈጸመው ድርጊት የተሰየሙ ሲሆን ከፊሎቹ ድርጊቱ በተፈጸመባቸው ቦታዎች ተሰይመዋል፡፡ በድርጊቱ የተሰየሙት ጽንሰት፣ ልደት፣ ጥምቀት፣ ስቅለት፣ ትንሣኤ፣ ዕርገት ሲሆኑ ሁለቱ ሆሳዕናና  ጰራቅሊጦስ ደግሞ ድርጊቱንና ስምን አስተባብረው የያዙ ሲሆን ከእነዚሁ ሁሉ ተለይቶ ደብረ ታቦር ድርጊቱ በተፈጸመበትDebre_Tabor ቦታ ተሰይሟል፡፡

 

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሁሉም ምሥጢራት ነገረ ምጽአቱንና ምሥጢረ መንግሥቱን በተራራ ላይ ገልጿል፡፡ ነገረ ምጽአትን በደብረ ዘይት የገለጸበትን ምክንያት ጠቢቡ ስሎሞን ለሁሉም ጊዜ አለው እንዳለ ለጊዜው ትተነው ወደ ደብረ ታቦር እንመለስ ፡፡ጌታችን ብርሃነ መለኮቱን ለደቀ መዛሙርቱ የገለጠበት ነቢያት ሊያዩት የተመኙትን ያዩበት ነቢያትና ሐዋርያት በአንድነት የተገናኙበት፣ ተገናኝተው እንደ አንድ ልብ መካሪ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ሆነው የክርስቶስን የባህርይ አምላክነት የመሰከሩበት፤ እግዚአብሔር ወልድ በክበበ ትስብዕትና በግርማ መለኮት የተገለጠበት፣ እግዚአብሔር አብ በደመና የምወደው ለተዋሕዶ የመረጥኩት በዕርሱ ህልው ሆኜ የምመለክበት ልጄ ይህ ነው እርሱን ስሙት ብሎ የመሰከረበት፣ መንፈስ ቅዱስም በአምሳለ ርግብ የወረደበት፣ እግዚአብሔር አንድነቱን ሦስትነቱን የገለጠበት እነ ቅዱስ ጴጥሮስ ለመኖር የተመኙት ደብረ ታቦር ነው፡፡ በዓሉ የጌታችን ሲሆን በስሙ ደብረ ታቦር ተብሏል፡፡ ይህን በዓል ስናከብር ያን ጊዜ ጌታችን ደቀ መዛሙርቱን አስከትሎ ወደ ተራራው ሲወጣ በተራራው ራስ ላይ ምሥጢሩን ሲገልጥላቸው አእምሮአቸውን ሲከፍትላቸው ከግርማው የተነሣ ፈርተው ሲወድቁ ሲያነሣቸው በዐይነ ሕሊና የምንመለከትበት ነው፡፡

 

ለዚህ ምሥጢር ደብረ ታቦር ለምን ተመረጠ?

1.    ደብረ ታቦር የድል ተራራ ነው፡፡

የእስራኤል ነቢይት ዲቦራ ለባርቅ የእስራኤል ጠላት የነበረው የኢያቢስን የሠራዊት አለቃ ሲሣራን ለመውጋት ወደ ደብረ ታቦር አስር ሺ ሰዎችን አስከትሎ እንዲወጣ ነግራዋለች፤ “የአቢኒኤምን ልጅ ባርቅ ጠርታ የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ሔደህ ወደ ታቦር ተራራ ውጣ ከአንተም ጋር ከንፍታሌምና ከዛብሎን ልጆች አስር ሺ ሰዎች ውሰድ” መሳ.4፥6፡፡ በዚህ መልኩ ባርቅ አስር ሺ ሰዎችን አሰልፎ ዲቦራን አስከትሎ በደብረ ታቦር ሰፍሮ የነበረውን የሲሣራን ሠራዊት ድል ነሥቶበታል፡፡ ሲሣራ ዘጠኝ መቶ የብረት ሠረገላ እንዲሁ ብዙ ሠራዊትም በታቦር ያሰለፈ ቢሆንም ድል ግን ረድኤተ እግዚብሔርን ጥግ ላደረገ ለባርቅ ሆነ፤ በዚህ ጊዜ ዲቦራ በታቦር ተራራ የሙሴ እኅት ማርያም በኤርትራ ባሕር የዘመረችውን መዝሙር የመሠለ ምስጋና አቅርባለች፡፡ ሁሉም እስራኤላውያን የድል መዝሙር ዘምረውበታል ፈጣሪአቸውን አመስግነውበታል፡፡ ጌታችንም የባሕርይ አምላክነቱን ገልጾ ከደቀ መዛሙርቱ ልቡና አጋንንትን የሚያባርርበት ዲያብሎስን ድል የሚነሳበት ስለሆነ ከሌሎች ተራሮች ተመርጧል፡፡

 

2.    ትንቢት ተነግሮለታል

“ታቦር ወአርሞንዔም በስመ ዚአከ ይትፌስሑ ወይሴብሑ ለስምከ” መዝ. 88፥12 ታቦርና አርሞንዔም በስምህ ደስ ይላቸዋል” ብሎ ቅዱስ ዳዊት ከክርስቶስ ሰው ሆኖ መገለጥ በፊት አምላካችን ክርስቶስ ብርሃነ መለኮቱን በደብረ ታቦር እንደሚገልጽ ብርሃኑ ከደብረ ታቦር እስከ አርሞንዔም ድረስ እንደሚታይ ይህም መለኮታዊ ብርሃን በታቦርና በአርሞንዔም ዙሪያ ለነበሩ ሕዝቦች ደስታ እንደሚሆን ተናግሯል፡፡ እንደሚታወቀው ታቦር የተባለው ተራራ ከገሊላ ባሕር በምዕራብ በኩል 10 ኪ. ሜትር ርቆ የሚገኝ ተራራ ሲሆን ተራራው እስከ 572 ሜትር ከባሕር ጠለል/ወለል ከፍ ይላል፡፡ ቀደም ሲል እንደገለጽነው ባርቅ ሲሣራን ድል ነሥቶበታል፤ የመጀመሪያው የእስራኤል ንጉሥ ሳዖል በሳሙኤል እጅ ተቀብቶ ሲመለስ ሦስት ሰዎች ታገኛለህ አንዱ ሦስት የድል ጠቦቶች ሁለተኛው ሦስት ዳቦ ይዟል፤ ሦስተኛውም የወይን ጠጅ አቆማዳ ይዟል፡፡ ሠላምታ ይሰጡሀል ብሎ ሳሙኤል ነግሮት ነበር፡፡ በነገረው መሠረት ሦስት ሰዎችን አግኝቶበታል፡፡ “ከዚያም ደግሞ ወደፊት ትሔዳለህ ወደታቦር ወደትልቁ ዛፍ ትደርሳለህ” 1ሳሙ.10፥3-5፡፡

 

ስለዚህ ተራራ ቅዱስ ዳዊት በድጋሜ እንዲህ በማለት ትንቢት ተናግሮለታል፡፡ “የእግዚአብሔር ተራራ የለመለመ ተራራ ነው፡፡ የጸና ተራራ የለመለመ ተራራ ነው፡፡ እግዚአብሔር ይህን ተራራ ያድርበት ዘንድ ወደደው” መዝ.67፥15 ብሎ እግዚብሔር ብርሃነ መለኮቱን እንደሚገልጥበት ዘምሮአል፡፡ በእነዚህ ከላይ በአየናቸው ሁለት ምክንያት ደብረ ታቦር ለዚህ ተመርጧል፡፡ወንጌላዊያኑ ቅዱስ ማቴዎስና ቅዱስ ማርቆስ ጌታችን ወደ ደብረ ታቦር የወጣው ደቀ መዛሙርቱን በቂሣርያ “ሰዎች የሰውን ልጅ ማን ይሉታል” ብሎ በጠየቃቸው በሰባተኛው ቀን ነው ብለው በቅዱስ ወንጌል የጻፉ ሲሆን ቅዱስ ሉቃስ በስምንተኛው ቀን ነው ይላል፡፡ ማቴ.17፥1-8፣ ማር.9፥2-8፣ ሉቃ.9፥28 ነገሩ እንዴት ነው? “እምድኅረ ሰዱስ መዋዕል ነሥኦሙ እግዚእ ኢየሱስ ለጴጥሮስ ወለ ያዕቆብ ወለ ዮሐንስ ዕሁሁ ወአፅረጎሙ ደብረ ነዋኅ እንተ ባህቲቶሙ” ከስድስት ቀን በኋላ ኢየሱስ ጴጥሮስንና ያዕቆብን ወንድሙንም ዮሐንስን ወደ ረጅም ተራራ ብቻቸውን አወጣቸው” ማቴ. 17፥1፣ ማር.9፥2፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ነገሩ እንደ ማቴዎስ ነው ብለው በሰባተኛው ቀን መሆኑን በትርጓሜያቸው አስቀምጠዋል፡፡ ታዲያ ስለምን ስምንት አለ? የሚለውን ሲያትቱ /ሲያብራሩ/ ስምንት ያለው ሰባት ሲል ነው ብለው ተርጉመውታል ምክንያቱም አንድ ሳምንት የሚባለው ሰባት ቀን ነው፡፡ ሊቁ ቅዱስ አትናቴዎስ ስለ ዕለተ ሰንበት ሲናገር ኦ ቅድስት ንዒ ኀቤነ ለለሰሙኑ ከመንትፈሣህ ብኪ ለዓለመ ዓለም” ቅድስት ሆይ በየሳምንቱ ወደኛ ነዪ በአንቺ ደስ ይለን ዘንድ ለዘለዓለሙ”  በማለት ሰሙን ማለት ስምንት ማለት ቢሆንም ሊቁ ግን ሳምንት ብሎት ይገኛል፤ ሳምንት ማለት ደግሞ ሰባት ቀን ነው ከዚህ የተነሣ ሉቃስ በሰባተኛው ቀን ያለው በሰባተኛው ሲል ነው፡፡ በሌላ መልኩ ማቴዎስ በሰባተኛው ቀን ሲል ሉቃስ በስምንተኛው ቀን ማለቱ የወጡበትንና የተመለሱበትን ቆጥሮ ነው፡፡ ከዚህ ባለፈ መጽሐፍ የጎደለውን ሞልቶ የሞላውን አትርፎ መናገር ልማዱ ነው ይህንም በሚከተሉት ማየት እንችላለን፡፡

 

ሰሎሞን “ወነበርኩ ውስተ ከርሰ ዕምየ አሠርተ አውርሀ ርጉኦ በደም” ጥበ.7፥2 “በእናቴ ማኅፀን በደም ረግቼ አሥር ወር ነበርኩ ብሏል ይህን ያክል ረጅም ቀን የመጨመር ልማድ ያለው መጽሐፍ በስምንተኛ ቀን ቢል ብዙ የሚደንቅ አይደለም የሚጣረስም አይደለም፡፡ የሚጣረሰው ወይም የሚጋጨው የእኛ አእምሮ ነው ከዕውቀት ማነስ ስለሆነ፡፡

 

ወበጽሐ ወርሀ ለኤልሳቤጥ” የኤልሳቤጥም የመውለጃዋ ወራት ደረሰ ሲል ቀን አልዘረዘረም ሰው የሚወለድበት ቀኑ የታወቀ ስለሆነ ነው፡፡ ሉቃ.1፥57 ስለ እመቤታችንም ሲናገር “በዚያ ሳሉም የመውለጃዋ ወራት ደረሰ የበኩር ልጅዋንም ወለደች” ሉቃ.2፥6 ወራት ሲል ከአንድ በላይ ሁለትም ሦስትም ወራት ይባላሉ አሁን ከዚህ የምናየው መጽሐፍ ጠቅልሎ ሲፈልግ ዘርዝሮ አስፈላጊ ሲሆን በአኀዝ ወስኖ ሲልም ጎድሎ አስፈላጊ ሲሆን ሞልቶ ሊናገር እንደሚችል ያስረዳናል፡፡ “ተፀውረ በከርሣ ፱ተ አውራሀ” ዘጠኝ ወር በማኅፀኗ አደረ” ወደ ማርያም በማኅፀኗ ያደረው ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን ሲሆን አምስት ቀን አጉድሎ ሲናገር እናገኘዋለን ከዚህ አንጻር ሉቃስም አንድ ጨምሮ ነው ስምንት ያለው መጨመር ማጉደል የመጻሕፍት ልማድ ነውና፡፡

 

ጌታችን በደብረ ታቦር ምሥጢረ መለኮቱን የገለጠው እንዴት ነው?

ይህንን ከማየት አስቀድሞ መገለጡ በምን ምክንያት ነው የሚለውን ማየቱ የተሻለ ነው፡፡ ብርሃነ መለኮቱን የገለጠው በሦስት ምክንያቶች ነው ነሐሴ ሰባት ቀን በቂሳርያ ደቀ መዛሙርቱን “ሰዎች የሰውን ልጅ ማን ይሉታል? ” ብሎ በጠየቃቸው ጊዜ ኤርምያስ ነው፣ ኤልያስ ነው፣ ዮሐንስ መጥምቅ ነው፣ ከነቢያት አንዱ ነው፣ ይሉሀል የሚል የተለያየ መልስ ተሰጥቶት “እናንተስ ማን ትሉኛላችሁ?” ባላቸው ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ “አንተ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ነህ” ብሎ መስክሯል፡፡

 

  1. በፍጡር ቃል የተመሰከረውን በባሕርይ አባቱ ለማስመስከር

  2. ከነቢያት አንዱ ነው ብለውት ነበርና እግዚአ ነቢያት /የነቢያት ጌታ/ እንደሆነ ለማስረዳት

  3. እሞታለሁ እሰቀላለሁ ሲል ጴጥሮስ “ሀሰ ለከ” ልትሞት አይገባህም ብሎት ነበርና እርሱን ስሙት ለማለት፡፡

 

በፍጡር በጴጥሮስ የተመሠከረውን ምስክርነት የባሕርይ አባቱ “ይህ የምወደው ልጄ ነው እርሱን ስሙት” ማለት እሞታለሁ እሰቀላለሁ ቢላችሁ አይገባህም አትበሉት ዓለም የሚድነው በእርሱ ሞት ነውና ተቀበሉት ለማለት ነው፡፡  ለጴጥሮስ መልስ እንዲሆን ይህ ሊሆንብህ አይገባም ብሎት ነበርና ያዕቆብና ዮሐንስም አንዳችን በቀኝህ አንዳችን በግራህ እንሾም ብለው ነበርና ፍቅረ ሲመትን ሊያርቅላቸው የእርሱን የባሕርይ ክብሩን አይተው የመጣለት ዓላማ ልዩ መሆኑን እንዲረዱ እነዚህን ሦስቱን ይዞ ወደ ተራራው ወጥቷል፡፡ ከነቢያት አንዱ ነው ብለውት ነበርና ከነቢያት ሙሴንና ኤልያስን በተራራው ተገኝተው እንዲመሰክሩ አድርጓል፡፡ ሙሴ ምነው የኔን የሙሴን አምላክ÷ አምላከ ሙሴ፣ እግዚአ ሙሴ ይበሉህ እንጂ ማነው ሙሴ የሚልህ፤ ኤልያስም የኔን የኤልያስን አምላክ÷ ኤልያስ የሚልህ ማነው? አምላከ ኤልያስ፣ እግዚአ ኤልያስ ይበሉህ እንጂ በማለት መስክረውለታል እንዴት ነው ምሥጢረ መለኮቱን የገለጠው የሚለውን ለማብራራትም ሆነ ለመተንተን ዕውቀትም ቃላትም ያጥረናል፡፡ ወንጌላውያን መግለጥ በሚችሉት መጠን ከገለጹት ያለፈ ልናብራራው የምንችለው አይደለም፡፡ ማቴዎስ እንዲህ ይገልጸዋል “ወተወለጠ ራዕዩ በቅድሜሆሙ ወአብርሀ ገጹ ከመ ፀሐይ ወአልባሲሆኒ ኮነ ፀአዳ ከመ በረድ” “በፊታቸውም ተለወጠ ፊቱም እንደ ፀሐይ በራ ልብሱም እንደ ብርሃን ነጭ ሆነ” ማቴ.17፥2 ብሎ ወንጌላዊው በዚህ ዓይነት ገለጾ የተናገረው ምሳሌ ስለ አጣለት ነው፡፡ ማርቆስም ይህንኑ ተጋርቶ “ልብሱን አንፀባረቀ አጣቢም በምድር ላይ እንደዚያ ሊያነጣው እስከማይችል በጣም ነጭ ሆነ” ማር.9፥2-4 “የፊቱ መልክ ተለወጠ ልብሱም ተብለጭልጮ ነጭ ሆነ” ሉቃ.9፥29-30፡፡ ከዚህ ወንጌላውያን ከገለጹበት የሚሻል ምሳሌ አናገኝለትም፡፡ በደብረ ታቦር ሐዋርያት ካዩት በተጨማሪ አብ በደመና ሆኖ የምወደው ልጄ ነው እርሱን ስሙት ሲል ተሰምቷል መንፈስ ቅዱስም በአምሳለ ርግብ ታይቶ አንድነት ሦስትነት ተገልጿል፡፡

 

ይህንን ኢትዮጵያዊቷ የቅኔ መምህርት እማሆይ ገላነሽ እንዲህ በማለት በቅኔአቸው ገልጸውታል፡፡

“በታቦርሂ አመቀነፀ መለኮትከ ፈረስ

ኢክህሉ ስሂቦቶ ሙሴ ወኤልያስ”

መለኮት ፈረስ በደብረ ታቦር በዘለለ ጊዜ ሙሴና ኤልያስ ሊስቡት አልቻሉም”

ብለው በምን አይነት ግርማ እንደተገለጸ ተቀኝተዋል፡፡

የደብረ ታቦር ባሕላዊ አመጣጥና ከመንፈሳዊው ሥርዓት ጋር ያለው ተዛምዶ፡-

ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ፣ “የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ” በሚል ርዕስ ባሳተሙት መጽሐፋቸው የደብረ ታቦር በዓል አከባበርን አስመልክቶ በሀገራችን ያለውን ሥርዓትና የትመጣነት እንደሚከተለው ጽፈውታል፡-

አስቀድመን እንደተመለከትነው ጌታችን በዚህ ዓለም እየተመላለሰ በሚያስተምርበት ጊዜ በደብረ ታቦር ብርሃነ መለኮቱን፣ ክብረ መንግሥቱን መግለጡን በማሰብ በየዓመቱ ነሐሴ 13 ቀን በዓሉ ይከበራል፡፡ ይህ በዓል በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በተለይም በምእመናን ዘንድ የተለየ ስም አለው፤ ይኸውም “ቡሄ” የሚለው መጠሪያ ስም ነው፡፡ ቡሄ ማለት /መላጣ ፣ ገላጣ/ ማለት ነው፡፡ በሀገራችን ክረምቱ፣ አፈናው ተወግዶ የብርሃን ወገግታ የሚታይበት በዚሁ በዓል አካባቢ ስለሆነ “ቡሄ” ያሉት ለዚሁ ሳይሆን አይቀርም፡፡ ድርጊቱ በተፈጸመበት በፍልስጥኤም ግን የደመና መልክ የማይታይበት ፍጹም የበጋ ወራት ነው፡፡ በሀገራችን ሕፃናቱ ይህ በዓል ከመድረሱ በፊት ቀደም አድርገው ጅራፍ ሲገምዱና ሲያጮሁ /ሲያኖጉ/ ይሰነብታሉ፡፡ እናቶችም ለዚህ በዓል የሚሆን ዳቦ ለመጋገር /የሚከበረው በዓል ነውና/ ስንዴያቸውን ሲያጥቡ፣ ሲፈትጉ ይሰነብታሉ፡፡ በዓሉ እንደነገ ሊሆን እንደ ዛሬ በዋዜማው /ነሐሴ 12/ የሠፈር ሕፃናት በየቤቱ እየዞሩ “ቡሄ ቡሄ” እያሉ ይጨፍራሉ፡፡ የሚገጥሙትም ግጥም አላቸው፡፡ “ቡሄ ና ቡሄ በሉ፤ ቡሄ መጣ፣ ያመላጣ ቅቤ ቀቡት እንዳይነጣ” እዚህ ላይ ቡሄ ያሉት ዳቦውን ነው፡፡ በዚህ ጊዜ እናቶች ካዘጋጁት ዳቦ እያነሱ ይሰጧቸዋል፡፡ ሄደው ዳቧቸውን እየገመጡ ሲጋረፉ ይውላሉ፡፡ ለግርፊያው ተምሳሌት ባይገኝለትም የጅራፉ መጮህ የድምፀ መለኮት ፣ጅራፉ ሲጮህ ማስደንገጡ የሐዋርያትን /የጴጥሮስን፣ የያዕቆብንና የዮሐንስን/ በድምፀ መለኮት መደንገጣቸውንና መውደቃቸውን ያስተውላል፡፡

በአንዳንድ ቀበሌዎች የቡሄ ዕለት ማታ ችቦ ያበራሉ፡፡ በደብረ ታቦር ለታየው ብርሃነ መለኮት ምሳሌ ነው፡፡ በዚያውም ላይ በኢትዮጵያችን የፀዓተ ክረምት ዋዜማ ስለሆነ ቡሄን ብርሃን ቢሉት ይስማማዋል፡፡ “ቡሄ ከዋለ የለም ክረምት ዶሮ ከጮኸ የለም ሌሊት” እንዲሉ፡፡ የቡሄ ዕለት ለዘመድ ለአዝማድ ለእያንዳንዱ ቤተሰብ በልጆቹ ልክ ዳቦ ይሰጣል፡፡ በተጨማሪም ለክርስትና ልጅ፣ ለአማች ለምራት፣ የቅርብ ዕውቂያ ላለውም ሁሉ የቡሄ ዳቦ ይሰጣል፡፡ በተማሪ ቤት ደግሞ ተማሪዎች ቀደም አድርገው “ስለደብረ ታቦር” እያሉ እህሉን፣ ጌሾውን ብቅሉን ይለምናሉ፤ ሕዝቡም ባሕሉን ስለሚያውቅ በገፍ ይሰጣቸዋል፡፡ የደብረ ታቦር ዕለት ጠላውን ጠምቀው ቆሎውን ቆልተው ዳቦውን ጋግረው ሊያስቀድሱ የመጡትን ምእመናን ሁሉ ከቅዳሴ በኋላ ይጋብዛሉ፡፡ ይህ እስከ አሁን በትምህርት ቤቶች የሚሠራበት ነባር ትውፊት ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

abune paulose

ስለ ቅዱስ ፖትርያርኩ ሥርዓተ ቀብር መግለጫ ተሰጠ

ሐሴ 12 ቀን 2004 ዓ.ም.

እንዳለ ደምስስ

መካነ ድራችን  በግልጥ ባልታወቀ ምክንያት የሲስተም ችግር ገጥሞት ስለነበር መረጃዎችን በወቅቱ ማድረስ ባለመቻላችን ይቅርታ እንጠይቃለን፡፡

የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፖትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ፕሬዚዳንት፣ የዓለም ሃይማኖቶች ለሰላም የክብር ፕሬዚዳንት ሥርዓተ ቀብር በማስመልከት ቅዱስ ሲኖዶስ መግለጫ ሰጠ፡፡

 

መግለጫውን የሰጡት ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል የቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት ዋና ጸሓፊ፣ የከፋ ቤንችና ማጂ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ሲሆኑabune paulose በመግለጫቸውም “ቅዱስነታቸው ሐሙስ ነሐሴ 10 ቀን 2004 ዓ.ም. ከንጋቱ 11፡00 ሰዓት ከዚህ ዓለም በሞተ ሥጋ መለየታቸውን በዕለቱ መግለጻችን ይታወቃል፡፡ በቀጣይነትም የቅዱስነታቸውን የቀብር ሥነ ሥርዓት አፈጻጸም ጊዜና ቦታ በተከታታይ የሚገለጽ መሆኑን በሰጠነው ማሳሰቢያ መሠረት የቀብር ሥነሥርዓቱ ሐሙስ ነሐሴ 17 ቀን 2004 ዓ.ም. በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል እንደሚፈጸም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡ እስከዚያው ድረስ ምእመናንና ምእመናት በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ በመገኘት ሃዘናቸውን መግለጽ የሚችሉ መሆኑን እንገልጻለን” ብለዋል፡፡

 

ስለ አሟሟታቸው ማብራሪያ እንዲሰጡ ከጋዜጠኞች ለቀረበላቸው ጥያቄም ቅዱስነታቸው ሱባኤውን ሳያቋርጡ እሑድ ቀድሰው ሰኞና ማክሰኞም ቅዳሴውን እየመሩ መገኘታቸውንና ከሰዓት በኋላ ህመም ስለተሰማቸወ ወደ ሕክምና መሔዳቸውን የገለጹ ሲሆን እረፍት እንዲያደርጉ በሐኪም ከተነገራቸው በኋላ በዚያው የእግዚአብሔር ጥሪ ሆኖ ሌሊት 11፡00 ሰዓት ላይ ማረፋቸውን ገልጸዋል፡፡ በተጨማሪም ስለ ቅዱስነታቸው ሕመም ሲያብራሩ “ብዙ ታመው ቤት አልዋሉም፡፡ ሥራም አላቋረጡም፣ ያልታሰበ ነገር ስለነበር በሞታቸው በጣም ተደናግጠናል፡፡ ሕመማቸው የስኳር ሕመም ጠንቅ ነው፡፡ ቀዶ ጥገናም አልተደገላቸውም በትናንትናው ዕለት እኔ ነኝ አጥቤ የገነዝኳቸው፡፡” በማለት ምላሽ ሰጥተዋል፡፡

የሥርዓተ ቤተ ክርስቲያኑ ቀኖና እንደሚያዘው አንድ ፖትርያርክ ሲያርፍ አቃቤ መንበር በዕለቱ መሠየም እንዳለበት ይገልጻልና ይህ ለምን ተፈጻሚ አልሆነም? ለሚለው ጥያቄ ምላሽ የሰጡ ሲሆን በጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ በፓትርያርኩ ጽ/ቤት ሓላፊ እንዲሁም በቅዱስ ሲኖዶስ ጸሐፊ አማካይነት ሥራዎች እንደሚከናወኑ፣ ከቅዱስ ፖትርያርኩ የቀብር ሥነ ሥርዓት በኋላ አቃቤ መንበር እንደሚሰይምና ይህም በመመካከርና በመስማማት ውሳኔውን መወሰናቸውን አብራርተዋል፡፡

 

ቅዱስ ሲኖዶስ ቤተ ክርስቲያኑን ለመምራት ምን ያህል ዝግጁ ነው? ለሚለው ጥያቄ ሲመልሱም “ይህ ጸሎት የሚጠይቅ ነው፡፡ እግዚአብሔር abune paulosእየረዳን፣ በምዕመናን ጸሎት እየተረዳን የተቻለንን ሁሉ እንጥራለን፡፡” ያሉ ሲሆን ከሰሜን አሜሪካ ካሉ አባቶች ጋር እየተካሄደ የነበረው እርቀ ሰላም እንደሚቀጥል አጽንኦት ሰጥተው ገልጸዋል፡፡

 

የቅዱስነታቸው የቀብር ቦታን አስመልክቶ እንዳልተናዘዙና በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ መሠረት ከልጅነታቸው ጀምሮ በቅስና እያሉ ባገለገሉበት፣ በተማሩበት፣ ከእስር ቤት ከተፈቱ በኋላ ክብር ባገኙበት በመንብረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል እንዲሆን ተወስኗል” ብለዋል፡፡

 

የቅዱስ ፖትርያርኩ ሥርዓተ ቀብር ዝርዝር መረጃም እንደሚከተለው ሰጥተዋል፡፡

  • ረቡዕ ነሐሴ 16 ቀን 2004 ዓ.ም. ከሰዓት በኋላ የቅዱስነታቸው አስከሬን ከመንበረ ፓትርያርክ በግልጽ ሠረገላ ወደ መንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ያመራል፡፡
  • ከምሽቱ 3፡00 ሰዓት ጀምሮ ጸሎተ ፍትሀት እየተከናወነ ያድራል፡፡
  • ሌሊት ሥርዓተ ቅዳሴ በሦስቱም መንበር በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ይቀደሳል፡፡
  • ከሥርዓተ ቅዳሴ በኋላ አስከሬናቸው ወደ ዐውደ ምሕረት በማውጣት ምዕመናን በተገኙበት ጸሎተ ፍትሀቱ ይቀጥላል፡፡
  • ከውጭ ሀገር የመጡ የአኀት ቤተ ክርስቲያናት ፖትርያርኮች ተገኝተው ንግግር ያደርጋሉ፡፡
  • የመንግሥት ባለ ሥልጣናት ንግግር ያደርጋሉ፡፡
  • የቅዱስነታቸው የሕይወት ታሪክ በቅዱስ ሲኖዶስ በተፈቀደላቸው ሊቀ ጳጳስ ይነበባል፡፡
  • አስከሬናቸው በቤተ ክርስቲያኑ ዑደት ያደርጋል፡፡
  • በመጨረሻም ሥርዓተ ቀብራቸው ይፈጸማል፡፡

 

picture1

ራሱን “ጉባኤ አርድእት ዘኦርቶዶክስ ተዋሕዶ” ብሎ የሚጠራውን ቡድን የቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት አገደ

ነሐሴ 9 ቀን 2004 ዓ.ም.

በዲ/ን አብርሃም አንዳርጌ

 

በጠቅላይ ቤተ ክህነት አካባቢ ራሱን “ጉባኤ አርድእት ዘኦርቶዶክስ ተዋሕዶ” ብሎ የሰየመውን ቡድን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት የእገዳ ደብዳቤ ጣለበት፡፡

 

የቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት የጉባኤው ዓላማና ፍላጎት ምን እንደሆነ እንደማይታወቅና እንዲህ ዓይነቱ ጉባኤ በቅዱስ ሲኖደስ ካለመቋቋሙም በላይ እውቅና ሳያገኝና ሳይፈቀድለት በራሱ ተነሳሽነት የሚንቀሳቀስ በመሆኑ የቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤትም የማያውቀውና ተቀባይነት የሌለው በመሆኑ በቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት ዋና ጸሓፊና የከፋ ሸካ ቤንች እና ማጂ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል ፊርማ ለመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት በቁጥር 486/836/2004 ሐምሌ 25 ቀን 2004 ዓ.ም. በተጻፈው ደብዳቤ መታገዱ ተገልጿል፡፡

 

“ጉባኤ አርድእት ዘኦርቶዶክስ ተዋሕዶ” በማለት ስለ ተቋቋመው ቡድን ያነጋገርናቸው የጠቅላይ ቤተ ክህነት አንዳንድ የመምሪያ ሓላፊዎች ቡድኑ በምን ምክንያት እንደተቋቋመና ለምንስ በኅቡዕ መንቀሳቀስ እንደፈለገ እንዳልተረዱ ጠቅሰው ጉዳዩን ለቤተ ክርስቲያኗ ደኅንነት ሲባል በአንክሮ እየተከታተሉ እንደሚገኙ ተናግረው በቤተ ክርስቲያኒቱ መዋቅር ውስጥ ሆነው የዚህን ሕገ ወጥ ቡድን አባላት በሆኑ ግለሰቦች ላይ ቀኖናዊና አስተዳደራዊ ርምጃዎች በቀጣይ እንደሚወስድም የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ምንጮች ገልጸውልናል፡፡

 

ጉባኤውን እያደራጁ የሚገኙ ግለሰቦች አብዛኛዎቹ በሚሠሩባቸው ቦታዎች ተቀባይነት እያጡ የመጡ ግለሰቦች እንደሆኑ የሚናገሩት የቤተ ክህነቱ ምንጮች ቅዱስ ሲኖዶስ እነዚህ ግለሰቦች ሊፈጥሩት ካሰቡት ከፍተኛ አደጋ ቤተ ክርስቲያኒቱን ሊታደጋት እንደሚገባ አመልክተዋል፡፡

 

የዚህ የእገዳ ደብዳቤ ግልባጭ ለብፁዕ ወቅዱስ ፓትሪያርክ ልዩ ጽ/ቤት፣ ለፌደራል ጉዳዮች ሚኒስቴር ለሃይማኖትና ሥነ ሥርዐት ዳይሬክቶሬት ጀኔራል፣ ለብሔራዊ ደኅንነትና መረጃ አገልግሎት፣ እንዲሁም ለፌደራል ፖሊስ ኮምሽን እና ለአዲስ አበባ ፖሊስ ኮምሽን ግልባጭ የተደረገ መሆኑን ለመረዳት ችለናል፡፡

 

picture1

የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ የ2004 ዓ.ም. እቅዶቹን በማጠናቀቅ ላይ እንደሚገኝ ገለጸ፡፡

ነሐሴ 8 ቀን 2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

 

በማኅበረ ቅዱሳን ትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ መርሐ ግብር በ2004 ዓ.ም. ሊያከናውናቸው ካቀዳቸው የአገልግሎት ዘፍፎች በአብዛኛው እያጠናቀቀ መሆኑን ገለጸ፡፡

 

የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ መርሐ ግብር ክፍል ሓላፊ የሆኑት ሊቀ ብርሃናት ሃይማኖት ተስፋዬ 2004 ዓ.ም. የክፍሉ የአገልግሎት አፈጻጸም አስመልክቶ እንደገለጹት “በታቀደው መሠረት በመላው ሀገሪቱ 200 የሕዝብ ጉባኤያትን 15 ሐዋርያዊ ጉዞዎችን ለማድረግ ታስቦ ሙሉ ለሙሉ ተግባራዊ ተደርገዋል፡፡ እንዲሁም በ10 ሀገረ ስብከቶች ውስጥ ለሚገኙ ካህናት የትምህርተ ኖሎትና የአስተዳደር የአሠልጣኞች ሥልጠና ለመስጠት ታስቦ በ8ቱ ሀገረ ስብከቶች ተተግብረዋል፡፡ በ10 ሀገረ ስብከቶች ውስጥ ለሚገኙ ሰንበት ትምህርት ቤቶች የተተኪ መምህራን ሥልጠና በታሰበው መንገድ ተሰጥቷል፡፡ ሰልጣኞቹም በየሀገረ ስብከታቸው በመንቀሳቀስ እያንዳንዱ ሀገረ ስብከት ሠላሳ ሠላሳ ሌሎች ሰልጣኞችን እንዲያሰለጥኑ በመደረግ ላይ ሲሆን ነሐሴ 16 ቀን 2004 ዓ.ም. ይጠናቀቃል ተብሎ ይጠበቃል” ብለዋል፡፡

 

የሰለጠኑት ካህናትና የሰንበት ትምህርት ቤት አባላት ወደታች ወርደው ሥልጠናውን ሲሰጡ ለመገምገም መቻሉን የገለጹት ሊቀ ብርሃናት ሃይማኖት ተስፋዬ “ሥልጠናው የካህናትና የተተኪ መምህራን ብቃት የሚያጎለብት እንደሆነ ጨምረው የገለጹ ሲሆን ሰንበት ትምህርት ቤቶች ያልተቋቋመባቸው ቦታዎች ላይ በማቋቋም የማጠናከሪያ አገልግሎት በመስጠት ወደተግባር መሸጋገራቸውን በተደረገወ ግምገማ ለማረጋገጥ መቻሉን ጨምረው ገልጸዋል፡፡

 

በ2005 ዓ.ም. ይህ አገልግሎት ተጠናክሮ የሚቀጥል ሲሆን የክፍሉ ሓላፊ ሊቀ ብርሃናትት ሃይማኖት ተስፋዬ ማኅበረ ቅዱሳን በግቢ ጉባኤያት ያሰለጠናቸው አቅም ያላቸው ተማሪዎችና ከመንፈሳዊ ኮሌጆች ትምህርታቸውን በመከታተል ላይ የሚገኙና የተመረቁ መምህራን ወደየመጡበት ሀገረ ስብከት በክረምቱ ስለሚሄዱ ሥልጠናዎችንና የስብከት አገልግሎት እንዲሰጡ በቅንጅት እየተከናወነ እንደሚገኝ አስታውቀዋል፡፡

 

ስላጋጠማቸው ችግር ሲገልጹም “ከፍተኛ ችግራችን የገንዘብና የመገልገያ ቁሳቁስ እጥረት ነው፡፡ በ2004 ዓ.ም. 10 የስብከት 10 የመዝሙር ካሴቶችንና በ4 የተለያዩ ቋንቋዎች መጻሕፍት ተዘጋጅተዋል፡፡ በኦሮምኛና በሲዳምኛ መዝሙር በኦሮምኛና በአማርኛ መጻሕፍት ተዘጋጅተዋል፡፡ እነዚህን ለምእመናን ለማዳረስ መታተም አለባቸው፡፡ ነገር ግን ዝግጅቶቹ ቢጠናቀቁም በገንዘብ እጥረት ምክንያት ሊሳካልን ባለመቻሉ በእጃችን ይገኛሉ፡፡ እነዚህንና ሌሎችም የስብከተ ወንጌል አገልግሎትን ለማስፋፋት እንድንችል ከ35 ሚሊዮን ብር በላይ ያስፈልገናል፡፡ ይህንንም ከበጎ አድራጊ ምእመናን እንጠብቃለን፡፡ በተጨማሪም የቢሮ መገልገያ ቁሳቁስ የተጠቀሙበትና የቀየሩት ኮምፒውተር፣ ፕሪንተርና ሌሎችም ድጋፍ ያደረጉ የገጠር ቤተ ክርስቲያናትን፣ የወረዳና ሀገረ ስብከቶችን ለማጠናከር ጠቀሜታ ስላላቸው ከምእመናን ብዙ ይጠበቃል በማለት ሊቀ ብርሃናት ሃይማኖት ተስፋዬ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡

ሀገረ ስብከቱ የ2004 ዓ.ም. ዕቅድ አፈጻጸምን ገምግሞ የአዲስ ዓመት ዕቅድን አጸደቀ፡፡

ነሐሴ 3 ቀን 2004 ዓ.ም.

ከጅማ ማእከል

  • ቅዱስ ሲኖዶስ ሕግ አውጥቶ ያዋቀረውን ማኅበር በአክራሪነት መፈረጅ ቤተ ክርስቲያንን መፈረጅ ነው፡፡

የጅማ ሀገረ ስብከት ጠቅላላ ጉባኤ የ2004 ዓ.ም. ዕቅድና ክንውንን በመገምገም፣ የ2004 ዓ.ም. ዕቅድን በማውጣትና መመሪያ በመቀበል ሰኔ 28-29 ቀን 2004 ዓ.ም. ተካሂዶ ተጠናቀቀ፡፡

 

ጉባኤውን የመሩት የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ ጠቅላላ ጉባኤው የ2004 ዓ.ም. የሥራ ግምገማ ማድረጉ ካለፈው ተሞክሮ በመውሰድ ለቀጣይ የተሻለ ለመሥራትና የቤተ ክርስቲያንን አገልግሎት ለማሻሻል የሚረዳ በመሆኑ በቀጣይም የተሳካ ሥራን ለመሥራት ሁሉም የበኩሉን እንዲወጣ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡

 

የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ መልአከ ብርሃን ስለሺ አስፋው ከ2004 ዓ.ም. የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት በተጨማሪ ሀገረ ስብከቱ የተዘጉ አብያተ ክርስቲያናትን ለማስከፈት ይረዳ ዘንድ እየተሠራ ያለው ባለ 5 ፎቅ ሕንፃ ግንባታን በተመለከተ የሒሳብ ራፖርት አቅርበዋል፡፡ ለዚህ ሥራም ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያበረከቱ አድባራትና ግለሰቦችን አመሰግነዋል፡፡

 

በጉባኤው ማጠቃለያ ላይም ብፁዕነታቸው ባስተላለፉት መልእክት በአንዳንድ ግለሰቦችና ድርጅቶች ቅዱስ ሲኖዶስ ሕግ አውጥቶ ያዋቀረውን ማኅበረ ቅዱሳንን በአክራሪነት ስም መፈረጅ ቤተ ክርስቲያንን መጥቀስ በመሆኑ ይህን የሚያደርጉ አንዳንድ አካላት ከድርጊታቸው መታረም እንዳለባቸው አሳስበዋል፡፡

 

በመጨረሻም በሀገረ ስብከቱ በበጀት ዓመቱ ብልጫ ሥራ የሠሩ አካላት የተሸለሙ ሲሆን የማኅበረ ቅዱሳን የጅማ ማእከል የዓመቱ ልዩ ተሸላሚ መሆኑን ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡

 

በሀገረ ስብከቱ በዘንድሮው ዓመት ከሁለት መቶ በላይ የሚሆኑ ወገኖች ከተለያዩ ቤተ እምነቶች ወደ ኦርቶዶክሰ ተዋሕኦ ሃይማኖት እንደተመለሰም በሪፖርቱ ተካቷል፡፡ የ2005 ዓ.ም. ጠቅላላ ጉባኤን በአጋሮ ከተማ እንዲዘጋጅ በመወሰን ጉባኤው ተጠናቋል፡፡

 

ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 19ኛ ዓመት ቁጥር 22 ከነሐሴ 1-15 ቀን 2004 ዓ.ም.