አርአያነት ያለው ተግባር

ነሐሴ 3 ቀን 2004 ዓ.ም.


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ


አሁን ያለው የክርስትናው ዓለም ከአለመኖር ወደ መኖር የመጣው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ዓለም አቀፍም፤ ሀገር አቀፍም መንፈሳዊ ተቋም በመሆን ስትፈጽመው በኖረችው ሐዋርያዊ አገልግሎት ነው፡፡ ይህን ዓለም አቀፍና ሀገር አቀፍ መንፈሳዊ አገልግሎት ስትፈጽም የኖረችበት ዘመንም በአኃዝ ሲቀመር ከሁለት ሺሕ ዓመታት በላይ አስቆጥሯል፡፡

 

ቤተ ክርስቲያን ከዚህ ዘመን የደረሰችው ያለ ርእይና ዕቅድ በዘፈቀደ በመጓዝ አይደለም፡፡ አባቶቻችን ዘመንን እየቀደሙ እያቀዱና እየተገበሩ፤ አተገባበራቸውንም እግዚአብሔርን አጋዥ አድርገው እየገመገሙ የተዛነፈውንም እያቀኑ ለቤተ ክርስቲያንም ሆነ ለትውልድ የሚሆነውን በጎ ነገር ሁሉ ሠርተው ቀምረው አስተላልፈዋል፡፡

 

ይህን የአባቶቻችን ዓቅዶ መሥራት፣ አፈጻጸሙን ቆም ብሎ ማየትን የሚዘክር ተግባር በጅማ ሀገረ ስብከት እያስተዋልን ነው፡፡ የሀገረ ስብከቱ ራስን የመገምገም ተግባርም ለሎሎችም አህጉረ ስብከት አርአያነት ያለው ነው፡፡

 

በአንዳንድ አህጉረ ስብከት እየደበዘዘ ወይም እየጠፋ ያለውን በዕቅድ መሥራትና አፈጻጸሙን የመገምገም ባህል ከማጎልበት አኳያ የጅማ ሀገረ ስብከት ተግባር ተስፋ ሰጪ ነው፡፡ ሀገረ ስብከቱ በየዓመቱ ጠቅላላ ጉባኤ ማካሔዱ ደግሞ ይበል የሚያሰኝ አካሄድ ነው፡፡

 

በዚህ ዓመታዊ ጠቅላላ ጉባኤ ላይ በሀገረ ስብከቱ ውስጥ የሚገኙ የወረዳ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጆች፣ የአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎች የሰበካ ጉባኤ አባላት፣ የሰንበት ትምህርት ቤቶች ተወካዮችና የማኅበራት ተወካዮች እንዲሳተፉ ከመደረጉም በላይ የእርስ በርስ የልምድ ልውውጥ መደረጉ በራሰ እጅግ ጠቃሚ መሆኑን እንገነዘባለን፡፡

 

ጠቅላላ ጉባኤው በጨዋነት፣ በመደማመጥና በመከባበር መንፈስ ችግሮችን ነቅሶ በማውጣት በግልጽ ተወያይቶ ለመፍትሔው ሁሉም የድርሻውን እንዲያበረክትና በጠቅላላ ጉባኤው የተላለፉትን ውሳኔዎች አተገባበር መከታተል መቻሉ፣ ያልተተገበሩ ሥራዎች ለምን አልተሠሩም ብሎ መጠየቅ ላይ መደረሱ፣ የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስም ሆኑ የሀገረ ስብከቱ ሠራተኞች በሥራቸው ያሉትን ካህናትንም ሆነ ምእመናንን ገንቢ ሂስ በሆደ ሰፊነት መቀበላቸው፤ ሌሎች አህጉረ ስብከት በአርአያነቱ ሊወስዷቸው የሚገቡ በጎ ተግባራት ናቸው እንላለን፡፡

 

በዕቅድ ተመርቶ መሥራትን፣ የዕቅድን አተገባበር መከታተልና የመቆጣጠርን አሠራርን ምን ታቀደ ምን ተሠራ ለምን አልተሠራም ብሎ የዓመቱን የአገልግሎት ጉዞ መለስ ብሎ መመልከትን እንደ ጅማ ሀገረ ስብከት ሁሉ ሌሎችም አህጉረ ስብከት ሊዘምቱበት ይገባል፡፡

 

ዐቅዳ የምትሠራ የሠራችውንም ሥራ ቆም ብላ የምትገመግም ቤተ ክርስቲያን፤ ምንም ጊዜ ቢሆን በየትኛውም ሁኔታ ድል አድራጊ ናት፡፡ ግልጸኝነትና ተጠያቂነትም ተቋማዊ መሠረት እንዲይዙ ያስችላታል፡፡ ለብልሹና አድሏዊ አሠራሮች የተጋለጡ የልማትም ሆነ አስተዳደራዊ ተቋማቶቿን ወደተሻለ ምዕራፍ እንድታሸጋግር ያግዛታል፡፡

 

ከዚህም በላይ ቤተ ክርስቲያናችን ተከታይይዋን ሕዝብ በሰበካ ጉባኤ በማደራጀትና በዚህም ውጤት በተገኘው የገቢ አቅም ጥንካሬ ስብከቷ፣ ትምህርቷ ሕልውናዋ ተጠናክሮ እንዲቀጥል፤ የቤተ ክርስቲያን ችግር ሆነው የኖሩትንም ሆነ የሚሆኑትን አጽራረ ቤተ ክርስቲያን ለመመከት የጅማ ሀገረ ስብከት አርአያነት ለትልቋ ቤተ ክርስቲያናችን ወሳኝ ነው፡፡

 

አጽራረ ቤተ ክርስቲያን ዛሬ ጉዟቸውን ወደ ቤተ ክርስቲያናችን በማድረግና በእኛዋ ቤተ ክርስቲያን ላይ ቀስታቸውን በማነጣጠር ወደ መንጋችን በረት ዘልቀው ለመግብት እያደረጉት ያለውን ሙከራ በሙከራ ደረጀ ለማስቀረት ብሎም እንዳይታሰብ ለማድረግ እንደ ጅማ ሀገረ ስብከት አቅዶ ለመሥራትንና አፈጻጸምን ገምግሞ ለቀጣይ ሥራ መዘጋጀት ይገባል እንላለን፡፡

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር


ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 19ኛ ዓመት ቁጥር 22 ከነሐሴ 1-15 ቀን 2004 ዓ.ም.

kidase

ጾመ ፍልሰታ

ነሐሴ 1 ቀን 2004 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ

እንኳን ለእመቤታችን ለቅድስት ድንግል ማርያም ጾመ ፍልሰታ በሰላም አደረሰን አደረሳችሁ፡፡ ፈጣሪያችን ጾሙን የበረከት፣ የረድኤት የንስሓ ያደርግልን ዘንድ ቅዱስ ፈቃዱ ይሁንልን፡፡ ንስሓ ገብተን፣ ጾመን ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን ተቀብለን ሕይወት እንድናገኝ የፈጣሪያችን ቸርነቱ አይለየን! አሜን

 

ጾም፡- መተውን መከልከልን መታቀብን፣ መታረምን የሚገልጥ የግብር ስም ነው፡፡

 

kidaseየቤተ ክርስቲያናችን የሥርዓትና የሕግ መጽሐፍ የሆነው ፍትሐ ነገሥት በ15ኛው አንቀጹ መግቢያ ላይ “ጾምስ በሕግ ውስጥ በታወቀው ጊዜ የሰው ከምግብ መከልከል ነው፡፡ በደሉን ለማስተሥረይ ዋጋውን ለማብዛት እርሱን ወዶ ሕጉን ለሠራለት እየተታዘዘ የፈቲዉን ኀይል ያደክምበት ዘንድ ለነባቢትም ነፍስ ትታዘዝ ዘንድ፤” በማለት የጾምን ምንነትና ጥቅም አጠር አድርጎ ያብራራል፡፡

 

ጾም ከመንፈሳዊ ተጋድሎዎች አንዱ ነው፡፡ ለሥጋም መንፈሳዊ ልጓም ነው፡፡ የሚጾም ሰው በጾም ፈቃደ ሥጋውን እየገታ ነፍሱን እንደሚጠቅም ይታወቃል፡፡ ስለዚህም ነው፡- “ከኀጢአት ፆር ከፍትወት አንዱንም ድል ለመንሣት ለማጥፋት በጾም መድከም የሥራ ሁሉ መጀመሪያ እንደሆነች የታወቀ ነው፡፡ የሥራ ሁሉ መጀመሪያ በጾም መድከም ነው፡፡ ይልቁንም በባሕርያችን የምትኖር ኀጢአትን ለሚዋጋ ሰው” በማለት ማር ይስሐቅ የተባለው መጽሐፋችን የሚናገረው፡፡ በማር ይስሐቅ አንቀጽ 4 ምዕራፍ 6 ላይ ጾምን በተመለከተ የሰፈረው መግለጫ “ጾም፡- የሥራ መጀመሪያ ናት፤ የጽሙዳን ክብራቸው ናት የድንግልና የንጽሕና ጌጻቸው ናት፤ የንጽሕና መገለጫ ናት፡፡ የወንጌል ሥራ መጀመሪያ ናት፡፡ የጸሎት ምክንያት ናት፡፡  የዕንባ መገኛ ናት፡፡ አርምሞን የምታስተምር ናት፡፡ ለበጎ ሥራ ሁሉ ታነቃቃለች” የሚለው ይገኝበታል፡፡

 

ከዚህ በላይ እንደተመለከተው ጾማችንን ከጸሎት ከምጽዋት ከሰጊድ እንዲሁም የጌታችን የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን በመቀበል ጭምር ልናስተሳስረው ይገባናል፡፡ አለዚያ ጾማችን ከእህልና ከውኃ ለተወሰነ ሰዓት ብቻ የምንከለከልበት ከሆነ እንደ ድልድይ ሆኖ ከፈጣሪያችን አያገናኘንም ግዳጅም አይፈጽምልንም፡፡ እንዲህ ተብሎ እንደተጻፈ፡- “ነገር ግን ዕለት ዕለት ይሹኛል መንገዴንም ያውቁ ዘንድ ይወድዳሉ፤ ጽድቅን እንዳደረጉ የአምላካቸውን ፍርድ እንዳልተዉ ሕዝብ እውነተኛውን ፍርድ ይለምኑኛል፥ ወደ እግዚአብሔርም ለመቅረብ ይወድዳሉ፡፡ ስለምን ጾምን ፥ አንተም አልተመለከትኸንም? ሰውነታችንንስ ስለምን አዋረድን፥ አንተም አላወቅህም? ይላሉ፡፡

 

እነሆ፥ በጾማችሁ ቀን ፈቃዳችሁን ታደርጋላችሁ፥ ሠራተኞቻችሁንም ሁሉ ታስጨንቃላችሁ፡፡ እነሆ ለጥልና ለክርክር ትጾማላችሁ በግፍ ጡጫም ትማታላችሁ፤… እኔ የመረጥሁት ጾም ይህ ነውን? ሰውስ ነፍሱን የሚያዋርደው እንዲህ ባለቀን ነውን? በውኑ ራሱን እንደ እንግጫ ዝቅ ያደርግ ዘንድ ማቅንና አመድንም በበታቹ ያነጥፍ ዘንድ ነውን? በውኑ ይህን ጾም ፥ በእግዚአብሔር ዘንድ የተወደደ ቀን ትለዋለህን? እኔስ የመረጥሁት ጾም ይህ አይደለምን? የበደልን እስራት ትፈቱ ዘንድ፥ የቀንበርንስ ጠፍር ትለቅቁ ዘንድ፥ የተገፋትንስ አርነት ትሰድዱ ዘንድ፥ ቀንበሩንስ ሁሉ ትሰብሩ ዘንድ አይደለምን? እንጀራህንስ ለተራበ ትቆርስ ዘንድ፥ስደተኞቹን ድሆች ወደ ቤትህ ታገባ ዘንድ፥ የተራቈተውንስ ብታይ ታለብሰው ዘንድ፥ ከሥጋ ዘመድህ እንዳትሸሸግ አይደለምን? የዚያን ጊዜ ብርሃንስ እንደ ንጋት ይበራል፥ ፈውስህም ፈጥኖ ይበቅላል፥ ጽድቅህም በፊትህ ይሄዳል፥ የእግዚአብሔርም ክብር በኋላህ ሆኖ ይጠብቅሃል፡፡ የዚያን ጊዜ ትጠራለህ እግዚአብሔርም ይሰማሃል ትጮኻለህ እርሱም እንሆኝ ይላል፡፡” /ትንቢተ ኢሳይያስ ምዕ.58፥2-9

 

ብሉይን ከሐዲስ አስማምታ የምትቀበል ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን የጾምንና የጸሎትን ሥርዓት ሠርታ እኛን ልጆቿን ለበረከት፣ ለሕይወት ለዘላለማዊ፣ ክብር ለማብቃት ታስተምረናለች፣ በሥርዓቷም ትመራናለች፡፡ በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ የጾም ዓይነቶች ሁለት ናቸው፡፡ እነርሱም የግል /የስውር/ እና የዐዋጅ አጽዋማት ይባላሉ፡፡

 

I.    የግል /የስውር/ ጾም

ምእመናን በልዩ ልዩ ምክንያት ከመምህረ ንስሓቸው ጋር በመመካከር በፍቃድ የሚጾሙት የጾም ዓይነት ነው፡፡ ይህም በሌላ አካል የማይታወቅና ሊታወቅ የማይገባ ነው፡፡ በንስሓ ምክንያት ከሚጾመው በተጨማሪ ስለቤተሰብ ስለወገን፣ ስለ ሀገር…. ወዘተ ተብሎ የሚጾሙት ጾም ይኖራል፡፡ ይህ ከዐዋጅ ጾም ከሚለይባቸው ምክንያቶች አንዱ በምሥጢር የሚጾም በመሆኑ ነው፡፡ በንስሐ ምክንያት ወይም በሌላ /በራሱ ፈቃድ የሚጾም ሰው መጾሙን ካሳወቀ እንደ ግብዝነት ከንቱ ውዳሴ ይሆንበታል፡፡ ይህ መሆኑም ዋጋ አያሰጠውም፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ስትጦሙም፥ እንደ ግብዞች አትጠውልጉ፤ ለሰዎች እንደ ጦመኛ ሊታዩ ፊታቸውን ያጠፋሉና፤ እውነት እላችኋለሁ ዋጋቸውን ተቀብለዋል፡፡ አንተ ግን ስትጦም፥ በስውር ላለው አባትህ እንጂ እንደ ጦመኛ ለሰዎች እንዳትታይ ራስህን ተቀባ ፊትህንም ታጠብ፤ በስውር የሚያይ አባትህም በግልጥ ይከፍልሃል፡፡” በማለት አስበ ጸሎታችንን /የጸሎታችንን ዋጋ/ ከፈጣሪ እንድናገኝ “እዩኝታን” /እዩልኝ፣ እወቁልኝ/ ከሚል የግብዝነት ሕይወት ተላቀን ልንጾመው እንደሚገባ አዞናል፡፡ /ማቴ.6፥16-18/

 

II.    የማኅበር /የዐዋጅ/ ጾም

በዐዋጅ ለሕዝቡ ተነግሮ ሕዝቡ ሁሉ ዐውቆት በአንድነት የሚጾም ጾም ነው፡፡ ሁሉም በአንድነት ወጥ በሆነ መልኩ የሚጾመው በመሆኑ ከንቱ ውዳሴ የለውም፡፡ ፈሪሳዊም አያሰኝም፡፡ በዐዋጅ ጾም አንድ ሰው እጾማለሁ ቢል በውስጡ እስካልታበየና እስካልተመካ ድረስ ጾምን ሰበከ ይባላል እንጂ ውዳሴ ከንቱ አምጥቶበት ዋጋ አያሳጣውም፡፡

 

በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ሥርዓት መሠረት ምእመናን ሁሉ እንድንጾማቸውና በሥጋም በነፍስም እንድንጠቀምባቸው መጀመሪያቸውና መጨረሻቸው ተቀምሮ ጊዜና ወቅት ተወስኖላቸው የተደነገጉ ሰባት የዐዋጅ አጽዋማት አሉ፡፡ እነዚህም በቅዱሳን አባቶቻችን በሐዋርያት ሲጾሙ የቆዩና ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን በቀኖና ያጸኗቸው ዲድስቅሊያና ሌሎች የቀኖና መጻሕፍት ሥርዓታቸውን የሠሩላቸው ናቸው፡፡ እንደ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በዓመት ውስጥ የሚጾሙት ሰባቱ አጽዋማት በጊዜ ቀደም ተከተላቸው መሠረት፡-

 

  1. ጾመ ነቢያት /ከኅዳር 15-ታኅሣሥ 29/
  2. ጾመ ነነዌ /ከጾመ ሁዳዴ መግቢያ 15 ቀን በፊት ያሉት ሦስት ቀናት ከሰኞ እስከ ረቡዕ/
  3. ጾመ ሁዳዴ /ከጾመ ነነዌ 15 ቀናት በኋላ፤ ለ55 ቀናት ይጾማል/
  4. ጾመ ገሃድ /የገና ዋዜማ እና ጥር 10 ቀን/
  5. ጾመ ድኅነት /ከበዓለ ሃምሳ በኋላ ከሚመጣው ረቡዕ ጀምሮ/
  6. ጾመ ሐዋርያት ከበዓለ ሃምሳ ማግስት ሰኞ ጀምሮ እስከ ሐምሌ 5/
  7. ጾመ ፍልሰታ /ከነሐሴ 1 እስከ ነሐሴ 14 ቀን፡፡

 

ከዚህ በላይ ከተዘረዘሩት አጽዋማት ለአሁኑ ጾመ ፍልሰታን እንመለከታለን

“ተንሥእ እግዚኦ ውስተ ዕረፍትከ አንተ ወታቦተ መቅደስከ፤ አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ፥ አንተና የመቅደስህ ታቦት” /መዝ.131፥8/

 

“ተንሥኢ ወንዒ ቅርብትየ እንቲአየ ሠናይት ርግብየ ውስተ ጽላሎተ ኰኲሕ ቅሩበ ጥቅም፡፡ አቅራቢያዬ መልካሟ ርግብየ ተነሽ፤ ነዪ፤ በግንቡ አጠገብ ወዳለው ወደ ዋሻው ጥላ፡፡” /መኃ.2፥10-14/

 

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እመቤታችንን መቅደሱ፥ ታቦቱ፣ ማደሪያው፣ መንበሩ እናቱ አድርጎ መረጣት፡፡ ስለዚህ ምክንያት አብ ጠበቃት ወልድ በተለየ አካሉ ሥጋን ከርሷ ተዋሐደ መንፈስ ቅዱስ አጸናት፡፡ እመቤታችን በዚህ ኃላፊ ዓለም ለ64 ዓመት ቆይታለች፡፡ ጥር ሰኞ ይብታል ሰኞ እስከ ሰኞ 8 ሰኞ እስከ ሰኞ 15፣ ሰኞ እስከ ሰኞ 22፣ ሰኞን ትቶ እሑድ ጥር 21 ቀን እመቤታችን አርፋለች፡፡ ሐዋርያት ባጎበር አድርገው ወደ ጌቴ ሴማኒ ይዘዋት ሲሄዱ አይሁድ “ቀድሞ ልጇን ሰቅለን ብንገድለው ደቀ መዛሙርቱ ተነሣ፣ ዐረገ” እያሉ ሲያውኩን ኖሩ፤ ዛሬ ደግሞ እርሷን ተነሣች፣ ዐረገች እያሉ ሊያውኩን አይደለምን? በእሳት እናቃጥላታለን” ብለው ተነሡ፡፡ ታውፋንያ የሚባል አይሁዳዊ ተራምዶ አጎበሩን ጨበጠው፡፡ መልአኩ ቅዱስ ሩፋኤል የታውፋንያን ሁለት እጁን በሰይፍ መትቶ ቀጣው፡፡ በዚህም የታውፋንያ ሁለት እጁ ከአጎበሩ ተንጠልጥሎ ቀረ፡፡ ከዚያ በኋላ መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌላዊውን ቅዱስ ዮሐንስ ጨምሮ በደመና ነጥቆ ከገነት በዕፀ ሕይወት ሥር አኖራት፡፡

 

ሐዋርያት ዮሐንስን “እንደምን ሆነች” አሉት፡፡ እርሱም፡- “በገነት ከዕፀ ሕይወት ሥር አለች” አላቸው፡፡ “ዮሐንስ አይቶ እኛ ሳናይ” ብለው፤ በነሐሴ መባቻ ጾም ጀመሩ፤ ሰኞ ነሐሴ 1 ቀን ጀምረው እሑድ ነሐሴ 14 ቀን ፈጽመዋል፡፡ በዚሁ ቀን ጌታችን ትኩስ በድን አድርጎ የእመቤታችንን ሥጋ ሰጥቷቸው ቀብረዋታል፡፡ እርሷም እንደ ልጇ በተቀበረች በሦስተኛው ቀን /ማክሰኞ/ ተነሥታ አርጋለች፡፡ “ከመ ትንሣኤ ወልዳ” ያሰኘውም ይህ ነው፡፡ በዚሁ ጊዜ ከሐዋርያት ወገን የሆነው ቅዱስ ቶማስ አልነበረም፡፡ ደመና ጠቅሶ ከሀገረ ስብከቱ /ከሕንድ/ ሲመጣ ስታርግ አገኛት፡፡ “ወፈቀደ ይደቅ እምደመናሁ” ይላል፤ ተበሳጨ፡፡ “ቀድሞ የልጅሽን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁ፤ ዛሬ ደግሞ ያንቺን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁኝ” አለ፡፡ በዚህ ጊዜ የልቡናን ሐዘን የምታቀል እመቤታችን፡- አይዞህ አትዘን እኒያ ትንሣኤዬን ዕርገቴን አላዩም፡፡ አንተ አይተሃል፡፡ ተነሣች፣ ዐረገች ብለህ ንገራቸው፡፡” ብላ የያዘችውን ሰበን ሰጥታ ሰደደችው፡፡ ከዚህ በኋላ ሄዶ፤ “የእመቤታችን ነገር እንደምን ሆነ?” አላቸው “ሥጋዋን አግኝተን ቀበርናት” አሉት፡፡ እርሱም “ሞት በጥር በነሐሴ መቃብር ተዉ ይህ ነገር አይመስለኝም” አላቸው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ “አንተ እንጂ ልማድህ ነው፡፡ አንተ ብቻ ተጠራጥረህ አትቀርም፤ አንተ እየተጠራጠርህ ሰውን ሁሉ ስታጠራጥር ትኖራለህ” አለው፡፡ እርሱም የያዘውን ያውቃልና ጸጥ ብሎ ይሰማቸዋል፡፡ ከዚህ በኋላ ቅዱስ ጴጥሮስ ተቆጥቶ ሂዶ መቃብሩን ቢከፍተው የእመቤታችን ሥጋዋን አጥቷል፡፡ በዚህም ምክንያት ደንግጦ ቆመ፡፡ ይህን ጊዜ ቅዱስ ቶማስ “አታምኑኝም ብዬ ነው እንጂ እመቤታችንስ ተነሣች ዐረገች” አላቸው፡፡ የያዘውንም ሰበን እያሳያቸው፡- “ቅዱስ ሥጋዋን የገነዛችሁበት ጨርቅ /ሰበን/ ይህ አይደለምን” ብሎ ሰበኑን ሰጣቸው፡፡ ይህንንም ለበረከት ተካፍለውታል፡፡ ከዚህ በኋላ በዓመቱ “ቶማስ ትንሣኤሽን ዕርገትሽን አይቶ እኛ ሳናይ በማለት ጾም ጀመሩ፡፡ በ16ኛው ቀን እመቤታችንን መንበር ቅዱስ ጴጥሮስን ንፍቅ ቄስ፣ እስጢፋኖስን ሠራዒ ዲያቆን አድርጎ ራሱ ቀድሶ አቁርቦአቸዋል፡፡

 

ስለዚህ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከጌታችን በኋላ ከክርስቲያኖች ሁሉ በፊት የትንሣኤንና የዕርገትን ክብር አግኝታ ልዑል እግዚአብሔር ባዘጋጀላት ልዩ ሕይወት እንደምትኖር ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ታስተምራለች፡፡

 

ምእመናን ሁላቸውም በየጾታቸውና በየመአረጋቸው ቀን በቅዳሴ፣ ሌሊት በሰዓታት በማኅሌት በኪዳን ቃለ እግዚአብሔርን በመስማትና ስብሐተ እግዚአብሔርን በማድረስ ይወሰናሉ፡፡

 

በእነዚህ አሥራ አምስት ቀናት የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ወላዲተ አምላክ ውዳሴዋና ቅዳሴዋ ተራ በተራ ይተረጎማሉ፡፡ ምእመናንም በፍቅርና በሃይማኖት የሚሰጠውን ትምህርት ይሰማሉ፡፡

 

ሶሪያዊው ቅዱስ ኤፍሬም እመቤታችንን ባመሰገነበት በውዳሴ ማርያም ድርሰቱ ከተናገራቸው ኀይለ ቃላት፡- “ነጸረ አብ እምሰማይ፡፡ ወኢረከበ ዘከማኪ፡፡ ፈነወ ዋሕዶ ወተሰብአ እምኔኪ፡፡ ማለትም እግዚአብሔር አብ በሰማይ ሆኖ አየ፤ አየና እንዳች ያለ ባያገኝ ተቀዳሚ ተከታይ የሌለውን ልጁን ወዳንቺ ላከው፡፡ ካንቺም ከሥጋሽ ሥጋ ከነፍስሽ ነፍስ ነሥቶ ሰው ሆነ፡፡” በማለት ያመሰገነበት ቃል ይገኛል፡፡ /ውዳሴ ማርያም ዘረቡዕ/ ይህ ቃል እመቤታችን ከፍጥረታት ሁሉ የከበረች በንጽሕናዋና በቅድስናዋ የተነሣ አምላክ ከእርሷ ተወልዶ /ሰው ሆኖ/ ዓለምን እንዲያድን ምክንያት የሆነችበትን ያስረዳል፡፡ በዳዊት መዝሙር ሰፍሮ በምናገኘው ቃል እግዚአብሔር አምላካችን የሚያስተውል እርሱንም የሚፈልግ ልብ ከሰዎች ልጆች እንዲያገኝ ቢመለከት አንዳች እንኳ እንዳጣና ሁሉ እንዳመፁ ተጠቅሶአል፡፡ /መዝ.13፥2-3/ ስለሆነም ነው ይህንኑ ቃል አባ ሕርያቆስ በቅዳሴው፡- “በአማን ነጸረ እግዚአብሔር አብ እምሰማይ ምሥራቀ ወምዕራበ ሰሜነ ወደቡበ፡፡ አስተንፈሰ ወአጼነወ፡፡ ወኢረከበ ዘከማኪ፡፡ ወሠምረ መዓዛ ዚአኪ፡፡ ማለትም እግዚአብሔር በልዕልና ሆኖ አራቱን ማዕዘን በእውነት ተመለከተ አስተናፈሰ አሸተተ ነገር ግን በንጽሕና በቅድስና የተዘጋጀች እንዳንቺ ያለች አላገኘም፡፡ መዓዛ ንጽሕናሽን መዓዛ ቅድስናሽን ወድዶ ለተዋሕዶ መረጠሽ፡፡” በማለት የተረጎመው፡፡

 

የተወደዳችሁ ምእመናን ለበረከት ይሆነን ዘንድ ከአባቶቻችን ቅዱሳን ሊቃውንት መካከል አንዱ የሆነው ቅዱስ ኤፍሬም ሶሪያዊ እመቤታችንን ካመሰገነበት የምስጋና ድርሰቱ አንዱን አንቀጽ እናንሣና ለአሁኑ እንሰነባበት፡፡

 

“ተፈሥሒ ኦ ወላዲተ እግዚእ ሐሤቶሙ ለመላእክት፡፡” የሚለው ቃል በቅዱስ ኤፍሬም የምስጋና ድርሰት ይገኛል፡፡ /የማክሰኞ ውዳሴ ማርያም/ ይህንን የምስጋና ድርሰት አባቶቻችን መምህራን እንዲህ ተርጉመውታል፡፡ “የመላእክት ደስታቸው የሚሆን ጌታን የወለድሽው ተፈሥሒ ደስ ይበልሽ፡፡ ለሊሁ ዓለሞሙ፣ ወለሊሁ ተድላሆሙ፣ ወለሊሁ ሀገሮሙ እንዲል፡፡ አንድም ሥጋዌውን ተልከው ለነቢያት የሚነግሩ መላእክት ናቸው፡፡ ከዚህ የተነሣ በአጭር ቁመት በጸባብ ደረት ተወስኖ አይተውት፤ ስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት ወሰላም በምድር ብለው አመስግነውት፤ በጣዕም ላይ ጣዕም በጸጋ ላይ ጸጋ ተጨምሮላቸው ደስ ብሏቸዋልና፡፡ አንድም የመላእክት ደስታቸው የምትሆኝ ጌታን የወለድሽው ተፈሥሒ ደስ ይበልሽ፡፡ ንጽሕናዋን ቅድስናዋን እያዩ ደስ ይላቸዋልና ሐሤቶሙ ለመላእክት አለ፡፡”

 

እንግዲህ ቅዱስ አባ ሕርያቆስ፡- “ኦ አንትሙ ሕዝበ ክርስቲያን ወበከመ ሰማዕክሙ ዘንተ ቃለ ቅዳሴሃ ለማርያም ከማሁ ያስምዕክሙ ቃለ መሰናቁት ዘሕፃናት” እንዳለው፤ ይህንን የእመቤታችንን ምስጋና ውዳሴ ለመስማት ለማንበብ ያበቃን ፈጣሪያችን በቸርነቱ ብዛት ከጣዕሙ ብዛት አጥንትን የሚያለመልም የመላእክትን ምስጋና የሕይወትን ቃል ያሰማን፡፡

 

ከእመቤታችን ከወላዲተ አምላክ ከድንግል ማርያም በረከት ረድኤት ያሳትፈን፡፡ ፍቅሯን በልባችን፣ ጣዕሟን በአንደበታችን ይሳልልን ያሳድርብን አሜን፡፡

hitsanat book large

ለሕፃናት

hitsanat book large

yseraamerare 005

ማኅበረ ቅዱሳን የ20 ዓመት ጉዞውን ሊገመግም ነው፡፡

ነሐሴ 1 ቀን 2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደጀኔ

ከ1984 ዓ.ም. ጀምሮ መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት እየሰጠ ያለው ማኅበረ ቅዱሳን ያሳለፋቸውን ሁለት ዐሥርት ዓመታት ጉዞውን የሚገመግም መሆኑ ተገለጸ፡፡

 

yseraamerare 005የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ ሊቀ ትጉኀን ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ሥዩም በነሐሴ ወር የሚደረገውን የማኅበሩን ጠቅላላ ጉባኤ አስመልክተው እንደገለጹት ማኅበረ ቅዱሳን ያከናወናቸው የ20 ዓመት ጉዞዎች በጠቅላላ ጉባኤው ላይ አንሥቶ እንደሚገመግም ገልጸዋል፡፡

 

ከ1986 ዓ.ም. ጀምሮ በየ2 ዓመት ጠቅላላ ጉባኤ ማድረግ መጀመሩን የገለጹት ሰብሳቢው ማኅበረ ቅዱሳን 20ኛ ዓመት የምሥረታ በዓሉን በሚያከብርበት ወቅት የሚካሄደው ጠቅላላ ጉባኤ ታሪካዊ ነው ብለዋል፡፡ ከነሐሴ 26-28 ቀን 2004 ዓ.ም. ለ3 ቀናት በሚዘልቀው ጉባኤ ቁጥራቸው ከአንድ ሺህ በላይ የሚሆኑ ተሳታፊዎች የሚገኙበት ሲሆን በዚህም ጉባኤ ከሀገር ውስጥና ከውጪ ማእከላት፣ ወረዳ ማእከላትና ግቢ ጉባኤያት የሚሳተፉበት እንዲሁም ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ ተጋባዥ እንግዶች የሚገኙበት መሆኑን አስታውቀዋል፡፡

 

ለ3 ቀናት በሚካሄደው 10ኛ ጠቅላላ ጉባኤ ቀጣይ የ4 ዓመት ስልታዊ እቅድ ከማጽደቅ ጀምሮ ቀጣዩን የአመራር ምርጫም እንደሚያደርግ ይጠበቃል፡፡

 

ለ10ኛ ጊዜ በሚደረገው ጠቅላላ ጉባኤ ከሀገር ውስጥ 44 ማእከላት፣ ከውጪ 9 ማእከላትና ግንኙነት ጣቢያዎች፣ 303 ወረዳ ማእከላት፣ እንዲሁም የግቢ ጉባኤያት ተወካዮች እንደሚገኙና ተጋባዥ እንግዶችን ጨምሮ ከአንደ ሺህ በላይ ተሳታፊዎች በጉባኤው ላይ ይታደማሉ፡፡

ሱባኤ፣ምንነቱ፣ሥርዓቱ

ሥርዓተ ሱባዔ

ሱባዔ ምንድን ነው? ሱባዔ በሰዋስው ትርጉሙ ሰባት ማለት ነው፡፡ ሱባዔ በመንፈሳዊ አተረጓጎም አንድ ሰው ከዚህ ቀን እስከዚህ ቀን በጸሎት ከፈጣሪዬ እገናኛለሁ ብሎ የሚያቅደው መንፈሳዊ ዕቅድ ነው፡፡ ሰባት ቁጥር በእስራኤላውያን ዘንድ በሥራም በቃልም የሚገለጥ ፍጹም ቁጥር ነው፡፡ ለምሳሌ፡- ፈጣሬ  ዓለማት እግዚአብሔር በሰባተኛው ቀን ሥነ ፍጥረትን ከመፍጠር ማረፉ፣ ለጸሎት የሚተጉ ምእመናን በቀን ለሰባት ጊዜ ማመስገናቸው የሰባት ቁጥርን ፍጹምነት ያመለክታል፡፡ ዘፍ.2፥2፤ መዝ.118፥64፡፡ ከዚህ አንጻር አንድ ሰው ለሰባት ቀናት ቢጾም «አንድ ሱባዔ ጾመ» ይባላል፡፡ ለዐሥራ አራት ቀን ቢጾም «ሁለት ሱባዔ ጾመ» እያለ እየጨመረ ይሄዳል፡፡

መቼ ተጀመረ?

ሱባዔ የተጀመረው ከውድቀት በኋላ በመጀመሪያው ሰው በአዳም ነው፡፡ ቅዱሳን መላእክት አዳምን ጸሎት መጸለይን እንዳስተማሩት የመጽሐፍ ቅዱስ ሊቃውንት ይናገራሉ፡፡ «መላእክት ለአዳም ጊዜያትን አስተምረውት ነበር፡፡» ቅዳሴ ማርያም ትርጓሜ፡፡ አዳም ጥፋቱን አምኖ ከባሕር ውስጥ ሱባዔ በመግባቱና በመጸለዩ እግዚአብሔር በማይታበል ቃሉ «ከአምስት ቀን ተኩል በኋላ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንኀለሁ» ሲል ቃል ኪዳን ገብቶለታል /መጽሐፈ ቀሌምጦስ አንቀጽ አራት/፡፡

ሱባዔ ለምን?

የሰው ልጅ ኃጢአት በሚስማማው የሥጋ ሰውነቱ ዘወትር ፈጣሪውን ይበድላል፡፡ በፈጸመው በደል ኅሊናው ይወቅሰዋል፡፡ ይጸጸታል፡፡ በመጀመሪያ ደፍሮ በሠራው ኃጢአት በኋላ ይደነግጣል፡፡ ይህ በማንኛውም ሰብአዊ ፍጥረት ኅሊና ውስጥ የሚፈራረቅ ክስተት ነው፡፡ በዚህ ጊዜ የፈጣሪውን ይቅርታ ለማግኘት ያስባል፤ ይተክዛል፡፡ «በውስጡ ሰውነቴ በእግዚአብሔር ሕግ ደስ ይለኛል. ነገር ግን በብልቶቼ ባለ በኃጢአት ሕግ የሚማርከኝ ሌላ ሕግ አያለሁ፡፡ እኔ ምንኛ ጐስቋላ ሰው ነኝ ለዚህ ሞት ከተሰጠ ሰውነት ማን ያድነኛል?» እንዳለ ቅዱስ ጳውሎስ፡፡ ሮሜ.7.22-25፡፡

ሰው በደፋርነቱ የኃያሉን አምላክ ትእዛዝ ተላልፎ ትካዜ ሽክም ሲያስጨንቀው ሸክሙን የሚያቃልልበትና የሚያስወግድበት መንፈሳዊ ጥበብ ከቸሩ ፈጣሪ ተሰጥቶታል፡፡ ይኸውም በጥቂት ድካመ ሥጋ ያልተወሰነ ጸጋ እግዚአብሔር የሚያገኝበት ሥርዓት ሱባዔ ነው፡፡ ከጥንት እስከ ዛሬ አንድ ሰው በትካዜ ሽክም መንፈሱ ሲታወክ የነፍስና የሥጋ ጸጥታውን ለመመለስና ለማስከበር መጾምና መጸለይ ግድ ይሆንበታል፡፡ በዚህ ጊዜ አመክሮ /ሱባዔ/ ይገባል፡፡

እግዚአብሔርን ለመማፀን

ሰው ሱባዔ ከሚገባባቸው መሠረታዊ ጉዳዮች አንዱ እግዚአብሔርን ለመማፀን ነው፡፡ ማንኛውም ሰው ሱባዔ ሲገባ በቁርጥ ወደ ፈጣሪው የሚያቀርበው ተማኅፅኖ ሊኖረው ይገባል፡፡ ምንም የምንጠይቀው /የምንማፀነው/ ነገር ሳይኖር ሱባዔ ብንገባ የምናገኘው መልስ አይኖርም፡፡ ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታና ዝግጅት ሱባዔ የሚገቡ ሰዎች ከሱባዔ በኋላ ምን እንደ ተመለሰላቸው የሚያውቁት ነገር ስለማይኖር ሱባዔ በመግባታቸው የሚያገኙት ነገር የለም፡፡

ስለዚህ ሱባዔ ከመግባታችን በፊት፡- «ሱባዔ የምገባው ለምንድን ነው?» በማለት ራሳችንን መጠየቅ ይኖርብናል፡፡ ለምሳሌ አንድ ክርስቲያን በግል ሕይወቱ ዙሪያ ስለ ሀገር ሰላም፣ ስለ ጓደኛው ጤና ወዘተ ጉዳዮች ላይ ፈጣሪውን ይማፀናል፡፡ በዚህ ጊዜ በግል ሕይወቱም ሆነ በሀገር ጉዳይ ለገባው ሱባዔ ወዲያውኑ መልስ ሊያገኝ ይችላል፤ እንዲሁም መልሱ ሊዘገይ ይችላል፡፡ በዚህ ጊዜ ከተሐራሚው ትዕግሥት /መታገሥ/ ይጠበቅበታል፤ «ለምን ላቀረብኩት ጥያቄ ቶሎ መልስ አልተሰጠኝ?» በማለት ማማረርና እግዚአብሔርን መፈታተን ተገቢ አይደለም፡፡ እግዚአብሔር ሥራውን የሚሠራበትና ለሚማፀነውም መልስ የሚሰጥበት የራሱ ጊዜ አለው፡፡ ለምሳሌ በጓደኛው ውድቀት ምክንያት ሱባዔ ገብቶ በአንድ ሳምንት ውስጥ መልስ ያገኘ የአንድ ገዳም አገልጋይ ታሪክ መመልከት ተገቢ ነው፡፡

«አኃው ለተልእኮ በወጡበት አንዱን ድቀት አግኝቶት አድሯል፡፡ በነጋው «ወንድሜ እኔ ድቀት አግኝቶኛልና እንግዲህ ወዲህ ተመልሼ ከዚያ ገዳም አልሔድም፤ ሽለሙን መስዬ እኖራለሁ» አለው፡፡ «እኔም እንጂ አግኝቶኛል፤ ይልቁንስ ሔደን ኃጢአታችንን ለመምህረ ንስሐችን ነግረን፤ ቀኖናችንን ተቀብለን እንደ ቀደመው ኾነን እንኖራለን» ብሎ አጽናንቶ ይዞት ሔደ፡፡ ሔደው ለመምህረ ንስሐቸው ነግረው ቀኖናቸውን ተቀብለው 1 /አንድ/ ሱባዔ፣ ቀኖና እንዳደረሱ «ሰረይኩ ለከ በእንተ ዘኢገብረ እኁከል፤ ኃጢአት ስላላደረገው ወንድምህ ይቅር ብዬሃለሁ» የሚል ድምፅ አሰምቶታል፡፡ /ዜና አበው/፡፡

ከላይ ታሪካቸው የሰፈረው የገዳም አገልጋዮች ለአገልግሎት በተላኩበት አገር አንዱ ድቀት አግኝቶት በዝሙት ሲወድቅ ጓደኛው እንደ እርሱ ድቀት እንዳገኘው አድርጐ ጓደኛውን በማጽናናት ወደ ገዳም በመመለስ አንድነት ኾነው ሱባዔ ይገባሉ፡፡ አንድ ሱባዔ /ሰባት ቀን/ እንደ ጨረሱ ከእግዚአብሔር ዘንድ «ኃጢአት ሳይሠራ ለአንተ ብሎ ሱባዔ ስለገባው ወንድምህ ስል ይቅር ብዬሃለሁ» የሚል ፈጣን መልስ አግኝቷል፡፡ ስለዚህ ሱባዔ በግል ሕይወትም ሆነ በጓደኛችን ሕይወት ዙሪያ ስንገባ ፈጣን ወይም የዘገየ መልስ ሊሰጠን ስለሚችል በትዕግሥት መጠባበቅ ይኖርብናል፡፡

የቅዱሳንን በረከት ለመሳተፍ

ቅዱሳን አባቶችና ቅዱሳት እናቶች የተጋደሉትን ተጋድሎ በማዘከር ቃል ኪዳን በተሰጣቸው ገዳማትና አድባራት የሚገባ ሱባዔ የቅዱሳኑን በረከት ተካፋይ ያደርጋል፡፡ ቅዱሳን በሚጋደሉበት ቦታ «ከወንዶችና ከሴቶች ልጆች ይልቅ የሚበልጥ ስም እሰጣቸዋለሁ፤ የማይጠፋ የዘላለም ስም እሰጣቸዋለሁ» /ኢሳ.56.6/ በማለት እግዚአብሔር ቃል ኪዳን ስለ ገባላቸው ሱባዔ በመግባት በረከታቸውን መሳተፍ ይቻላል፡፡ በጾመ ነቢያት የነቢያትን በረከት ለመሳተፍ፣ በጾመ ሐዋርያት የሐዋርያትን በረከት ለመሳተፍ፣ በጾመ ፍልሰታ የእመቤታችንን በረከት ለመሳተፍ ሱባዔ መግባት የነበረና ወደ ፊትም የሚኖር የቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ነው፡፡ ዛሬ ይህን ሥርዓት በመከተል የተለያዩ ቅዱሳንን በረከት ለመቀበል /ለመሳተፍ/ የቅዱሳን አፅም ካረፈበት ገዳም በጾም፣ በጸሎት፣ በጉልበትም ገዳማትን በማገልገል የቅዱሳንን በረከት ደጅ የሚጠኑ ምእመናንና መናንያን በየገዳማቱ እጅግ በርካታ ናቸው፡፡

ይኸውም በመጽሐፈ ነገሥት ካልዕ በምዕራፍ 2.9 እንደ ተመለከተው ነቢዩ ኤልሳዕ መምህሩን ኤልያስን በማገልገል የኤልያስ በረከት በእጥፉ በኤልሳዕ ላይ አድሮበታል፡፡ ይህን አብነት በማድረግ በየገዳማቱ በትሕርምት የሚኖር መናንያንን ያገለገሉበትን ገዳም አባት በረከት በእጥፍ እየተቀበሉ ለሌሎችም የሚያቀብሉ አባቶች በየገዳማቱ አሉ፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ሆኖ በስመ ገዳማዊ የምእመናንን ገንዘብ የሚዘርፉና የእውነተኛ መነኮሳትንና መናንያንን የተቀደሰ ሕይወት የሚያጐድፉ መኖራቸውን መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡

የተሰወረ ምሥጢር እንዲገለጥልን

በዘመነ ብሉይ እግዚአብሔር ለአንዳንድ ነገሥታት ራእይ በማሳየት ምሥጢርን ይሰውርባቸው ነበር፡፡ ለምሳሌ የግብፁን ፈርዖን፣ የባቢሎኑን ናቡከደነፆርንና ብልጣሶርን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ዘፍ.41.14-36፡፡ ዳን.4.9፤ ዳን.5.4፡፡ እነዚህ ነገሥታት በግል ሕይወታቸውም ሆነ በመላው ሽክም ወደ ፊት ሊፈጸም የሚችል ራእይ ቢያዩም ቅሉ ራእዩን በትክክል ተረድተው «እንዲህ ይሆናል» የማለት ብቃት አልነበራቸውም፡፡ ስለዚህ በዘመናቸው ይኖር የነበሩትን ነቢያት ሱባዔ ገብተው የሕልማቸውን ትርጉም እንዲነግሩአቸው ይማፀኑ ነበር፡፡ ነቢያትም ሱባዔ በመግባት ነገሥታቱ ያዩትን የምሥጢረ ሥጋዌ ነገርና የመንግሥታቸውን አወዳዳቅ ገልጸው ይናገሩ ነበር፡፡ ዳን.5.28፡፡

እንዲሁም ቅዱሳን በየራሳቸው ያዩት ራእይ ምሥጢር ሲከደንባቸው የራእዩ ምሥጢርና ትርጉም እንዲገለጥላቸው ሱባዔ ይገባሉ፡፡ እግዚአብሔርም በንጽሕና ሆነው የገቡትን ሱባዔ ተመልክቶ ምሥጢር ይገልጥላቸዋል፡፡ ለምሳሌ ነቢዩ ዕዝራ የመጻሕፍትን ምሥጢር እንዲገልጥለት ሱባዔ ቢገባ የጠፉትን የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ዳግም መልሶ ለመጻፍ ችሏል፡፡ መዝ.8.1፡፡

በዘመነ ሐዲስ በሰፊው የሚወሳው ቅዱሳን ሐዋርያት ከነሐሴ 1-14 የገቡት ሱባዔ ነው፡፡ ይህ ሱባዔ ተሰውሮ የነበረውን የቅድስት ድንግል ማርያምን ትንሣኤ ተረድተው በረከቷን ለመሳተፍ አብቅቷቸዋል፡፡

«እመቤታችን ያረፈችው ጥር 21 ቀን 50 ዓመተ ምሕረት ነው፡፡ ሐዋርያት ሊቀብሯት ወደ ጌቴ ሰማኔ ይዘዋት ሲሄዱ አይሁድ በታተኗቸው፡፡ በዚህ ጊዜ ቅዱሳን መላእክት የእመቤታችንን ሥጋዋን ወስደው በገነት ከዕፀ ሕይወት ሥር አኑረውታል፡፡» /ተኣምረ ማርያም፤ ስንክሳር ነሐሴ 16 ቀን/፡፡ በዚህ ጊዜ እነርሱ ተደናግጠው ስለተበታተኑ የእመቤታችን የዕረፍቷ ያስጨንቃቸው ነበር፡፡
«ቅዱስ ዮሐንስ በተመስጦ እየሄደ ሥጋዋን ያጥን ነበር፡፡ ለሐዋርያት ይህን ይነግራቸዋል፡፡ ለዮሐንስ ተገልጣ ለእኛ ሳትገለጥ ብለው በነሐሴ ሱባዔ ገቡ፡፡ ሁለተኛው ሱባዔ ሲፈጸም በ14ኛው ቀን መልአክ ሥጋዋን አምጥቶ ሰጥቶአቸዋል፤ ቀብረዋታል፡፡ በሦስተኛው ቀን ነሐሴ 16 ቀን ተነሥታ ዐርጋለች፡፡ /ተኣምረ ማርያም፤ ስንክሳር ነሐሴ 16 ቀን/፡፡

እንግዲህ ለቅዱሳን ሐዋርያት የእመቤታችን የዕረፍትና የዕርገት ምሥጢር የተገለጠላቸው በሱባዔ ነው፡፡ ይህን መሠረት በማድረግ ሐዋርያዊት ቤተ ክርስቲያን የእመቤታችንን የዕርገቷን በረከት ለማግኘት ትጾማለች፡፡ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ይህን የሱባዔ ወቅት ሕፃናትም ሳይቀሩ ይሳተፉታል፡፡

ሱባዔ ነቢያት

እግዚአብሔር ለአዳም የገባውን ቃል ኪዳን መሠረት በማድረግ ቀደምት ነቢያት በተነሡበት ዘመን ቅደም ተከተል ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው መሆንና ዳግም መምጣት ትንቢት ተናግረዋል፡፡ ሱባዔም ቆጥረዋል፡፡ ኢሳ.7.14፡፡ መዝ.49.3፡፡ ዘካ.13.6፤ ዘካ.14.1፡፡ የአንዱ ነቢይ ትንቢታዊ ንግግርና ሱባኤ በአነጋገርና በአቆጣጠር ከሌላኛው ነቢይ ጋር ይለያያል፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሔር ትንቢቱን ሲያናግር ምሳሌውን ሲያስመስል ጐዳናው ለየቅል በመሆኑ ነው፡፡ «ከጥንት ጀምሮ እግዚአብሔር በብዙ ዓይነትና በብዙ ጐዳና ለአባቶቻችን በነቢያት ተናገረ፡፡» እንዲል፡፡ ዕብ.1.1፡፡ የአቆጣጠር ስልታ ቸውና የሱባዔ መንገዳቸው ቢለያይም ዓላማና ግባቸው ግን አንድ ነው፡፡

ሱባዔ አዳም

አዳም ትንቢት በመናገርና ሱባዔ በመቁጠር የመጀመሪያውን ሥፍራ ይይዛል፡፡ ምክንያቱም በገነት ሰባት ዓመት ከአንድ ወር ከዐሥራ ሰባት ቀን በተድላና በደስታ ከኖረ በኋላ ሕግ በማፍረሱና የፈጣሪውን ቃል በመጣሱ ያለምንም ትካዜና ጉስቁልና ከሚኖርበት ዔደን ገነት ተባርሯል፡፡ ዘፍ.3.24፡፡ እርሱም ፈጣሪው እንዲታረቀው፣ በዐይነ ምሕረት እንዲጐበኘው፣ ቅዝቃዜው ሰውነት ከሚቆራርጥ ባሕር ውስጥ በመቆም ለሠላሳ አምስት ቀን /አምስት ሱባዔ/ ሱባዔ ገብቷል፡፡ በባሕርዩ የሰውን ልጅ እንግልት የማይወድ ቸሩ ፈጣሪ የአዳምን ፈጽሞ መጸጸት ተመልክቶ «በኀሙስ ዕለት ወበመንፈቃ ለዕለት እትወለድ እምወለተ ወለትከ ወእድኅክ ውስተ መርህብከ ወእቤዝወከ በመስቀልየ ወበሞትየኸ በአምስት ቀን ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ» ብሎ ተስፋውን ሰጠው፡፡ አዳም የተሰጠውን ተስፋ ይዞ በዓለመ ሥጋ ለዘጠኝ መቶ ሠላሳ አመት ከኖረ በኋላ መከራና ችግር ከበዛበት ዓለም በሞት ተለይቷል፡፡

በወንጀል ተከሶ በወኅኒ የተፈረደበት ሰው ከእስር የሚፈታበትን ዕለት በማውጣት በማውረድ ወራቱንና ዓመታቱን እንደሚቆጥር፣ አዳምም በሞት ቢለይም በሲኦል የነፍስ ቅጣት ካለበት ሥፍራ ይኖር ስለነበር የተሰጠውን ተስፋ በማሰብ ሱባዔውን እየቆጠረ የተናገረውን የማያስቀር የማያደርገውን የማይናገር ጌታየ «እነሆ አድንኀለሁ» ብሎ የገባልኝ ዘመን ተፈጸመ፤ ሰዓቱ አሁን ነው፤ እያለ ሲያወጣ ሲያወርድ ቸር አምላክ ሰው ኾኖ ሥጋ ለብሶ በአካለ ነፍስ ወደ ሲኦል ወርዶ፡- «ተንሥኡ ለጸሎት ለጸሎት ተነሡ፤ ሰላም ለኩልክሙ፤ ሰላም ለእናንተ ይሁን» በማለት አዳምን ከነልጅ ልጆቹ ነጻ አውጥቶታል፡፡ አዳምን በመከተል ልጆቹም አበው ቅዱሳን ነቢያት ሱባዔ በመግባት የተስፋን ዘመን በመቁጠር በመልካም ግብር ተከትለውታል፡፡ በዚህም መሠረት በርካታ ነቢያት በተለያየ ስልት ሱባዔ ቆጥረዋል፤ እኛም ሱባዔ ከቆጠሩ ነቢያት የተወሰኑትን በዚህ ጽሑፍ እንደሚከተለው እናቀርባለን፡፡

ሱባዔ ሔኖክ

ጻድቁ ሔኖክ፣ የያሬድ ልጅ ሲሆን፣ በትውልድ ከአዳም ሰባተኛ ነው፡፡ እርሱም በሕይወቱ እግዚአብሔርን ደስ ለማሰኘት ቤት ንብረቱን በመተው በሱባዔና በትሕርምት እግዚአብሔርን አገልግሏል፡፡ ፍጹም አካሔዱን ከእግዚአብሔር ጋር ያደረገ ሰው በመሆኑ በብሉይ ኪዳንም ሆነ በሐዲስ ኪዳን መልካም ግብር ተመስክ ሮለታል፡፡ «ሔኖክም አካሄዱን ከእግዚአብሔር ጋር አደረገ፡፡» ዘፍ.5.22፡፡ ይህም በመሆኑ እግዚአብሔር የሱባዔውን ዋጋ ቅዱስ መንፈሱን በረድኤት ስለ አሳደረበት ትንቢት ተናግሯል፤ ሱባዔ ቆጥሯል፡፡ በሰማይ ተሰውሮ ሳለ ስለ ቅዱሳን መላእክት፣ ስለ መሲሕ ኢየሱስ ክርስቶስ፣ ስለ ፀሐይና ጨረቃ አመላለስ /ዑደት/ የሚተርክ በስሙ የተሰየመውን መጽሐፍ ጽፏል፡፡ ዘፍ.5 21-24፡፡ ይሁዳ ቁ.14፡፡ ሔኖክ 1.9፡፡

ሱባዔ ሔኖክ የሚባለው ነቢዩ ሔኖክ በመስፈርት የቆጠረው ሱባዔ ነው፡፡ መስፈርቱ /ማባዣ ቁጥር/ 35 ሲሆን 35’19 ሲበዛ በውጤቱ 685 ዓመት ይሆናል፡፡ 685’12 ስናባዛው 7980 ይሆናል፡፡ ይኸውም ሐሳብ የሚያስረዳው ስለክርስቶስ ምጽአት ነው፡፡

ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ አሁን የደረስንበት ዘመን 7497 ይሆናል፡፡ ይህን ለማረጋገጥ በ5500 ዓመት ላይ 1997 ዓመትን መደመር ነው፡፡ በዚህን ጊዜ ከላይ ያስቀመጥነውን 7497 ዓመት ይሰጠናል፡፡ በነቢዩ ሔኖክ አቆጣጠር መሠረት ምጽአተ ክርስቶስ በ7980 ይሆናል፡፡ ከላይ ሔኖክ የቀመረውን ቁጥር ይዘን ከ7980 ዓመት ላይ አሁን ያለንበትን ዘመን /1997/ ስንቀንስ 483 ዓመት እናገኛለን፡፡ ስለዚህ በሔኖክ ሱባዔ መሠረት ምጽአተ ክርስቶስ ሊሆን 483 ዓመት ይቀራል፡፡

ሱባዔ ዳዊት

ነቢዩ ዳዊት ከእስራኤል ነገሥታት ሁሉ ታላቅና ተወዳጅ ንጉሥ ነበር፡፡ ዘመነ መንግሥቱ 1011-971 ከክርስቶስ ልደት በፊት እንደ ነበር ይታመናል፡፡ ነቢዩ ዳዊት ልበ አምላክ እንደ መሆኑ ትንቢት ተናግሯል፡፡ ሱባዔ ቆጥሯል፡፡ ይኽውም ቀመረ ዳዊት በመባል ይታወቃል፡፡ «እስመ ዐሠርቱ ምእት ዓመት በቅድሜከ፤ ከመ ዕለት እንተ ትማልም ኃለፈት፤ ሺ ዓመት በፊትህ እንዳለፈች እንደ ትላንት ቀን»፡፡ /መዝ.89.4/ የሚለውን መምህራን ሲቆጥሩት 1140 ዓመት ይሆናል፡፡ ይኸውም በጌታ ዘንድ 1140 ዓመት እንደ አንድ ቀን እንደሆነ ነቢዩ ዳዊት ተናግሯል፡፡ ይህም ለዳዊት ሱባዔ መቁጠሪያ /መሥፈሪያ/ ሆኖ አገልግሏል፤ 1140’7= 7980 ዓመት ይሆናል፡፡ ይህም ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ በ7980 ዓመት ክርስቶስ ዳግም እንደ ሚመጣ የሚያመለክት ነው፡፡

ሱባዔ ዳንኤል

ነቢዩ ዳንኤል ምድቡ ከዐበይት ነቢያት ነው፡፡ እስራኤል ወደ ባቢሎን ሲማረኩ ተማርኮ ወደ ባቢሎን ወርዷል፡፡ እርሱም ስለ ክርስቶስ መምጣት ትንቢት ተናግሯል፤ ሱባዔም ቆጥሯል፡፡ «ሰብአ ሰንበታተ አድሞሙ ለሕዝብከ፤ ሰባ ሰንበት ወገኖችህን ቅጠራቸው፡፡» ይኸውም ክርስቶስ ከ490 ዓመት በኋላ ሰው መሆኑን የሚያመለክት ትንቢት ነው፡፡ እንዲሁም «እስከ ክርስቶስ ንጉሥ ትትሐነፅ መቅደስ ወእምዝ ትትመዘበር፤ እስከ ንጉሥ ክርስቶስ ድረስ መቅደስ ትታነፃለች በኋላም ትፈርሳለች» ሲል ተናግሯል፡፡

የአቆጣጠር ስልቱም በዓመት ሲሆን ይኸውም ሰባቱን ዓመት አንድ እያሉ መቁጠር ነው፡፡ ይኽውም ሱባዔ ሰንበት ይባላል፡፡ ዳንኤል ሱባዔ ከቆጠረበትና ትንቢት ከተናገረበት ጀምሮ ክርስቶስ እስከ ሚወለድ 490 ይሆናል፡፡ መስፈርቱ /ማባዣው/ ሰባት ስለሆነ 7’70 ስናባዛው 490 እናገኛለን፡፡ ይኸውም ነቢዩ ሱባዔ ከቆጠረና ትንቢት ከተናገረ ከ490 ዓመት በኋላ የክርስቶስን መወለድ ያመለክታል፡፡

በአጠቃላይ ከላይ የተመለከትናቸው ቅዱሳን ነቢያት አካሄዳቸውን ከእግዚአብሔር ጋር በማድረግ ሱባዔ ገብተው በትሕርምት በመኖራቸው ድንቅ የሆነውን የክርስቶስን ልደትና ዳግም ምጽአት ለመተንበይ ችለዋል፡፡ ሱባዔ መግባት የራቀን ለማቅረብ የረቀቀን ለማጉላት ብቃትን ከእግዚአብሔር ዘንድ የሚያስገኝ መንፈሳዊ ጥበብ መሆኑን መገንዘብ ተገቢ ነው፡፡

የሱባዔ ዓይነቶች

  • የግል ሱባዔ/ዝግ ሱባዔ/

የግል ሱባዔ አንድ ሰው ብቻውን ሆኖ በቤትና በአመቺ ቦታ የሚይዘው ማንም ሰው ሳያየው በግሉ የጸሎት በኣቱን ዘግቶ በሰቂለ ኅሊና ሆኖ ፈጣሪው ብቻ እንዲያየው እንዲሰማው በኅቡዕ የሚፈጽመው ሱባዔ ነው፡፡ ማቴ.6፡5-13፡፡ በዚህ ዓይነት መልክ አንድ ሰው ሱባዔ ሲገባ ዘጋ ይባላል፡፡ ዝግ ሱባዔ የያዘ ሰው የሚያስፈልገውን ነገር ይዞ ወደ በኣቱ ከተከተተ በኋላ ሱባዔው እስኪፈጸም ድረስ ከሰው አይገናኝም፡፡ መዝ. 101-6-7፡፡

  • የማኅበር ሱባዔ

የማኅበር ሱባዔ የሚባለው ካህናት፣ ምእመናን ወንዶችና ሴቶች፣ ሽማግሌዎችና ወጣቶች በአንድ ሆነው በቤተ ክርስቲያንና አመቺ በሆኑ ቦታዎች ሁሉ ተሰብስበው የሚገቡት ሱባዔ ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን የነበሩ ምእመናን ወደ እግዚአብሔር በመሄድ ይጸልዩ ነበር፡፡ 1ኛ ሳሙ.1፡9፤ መዝ.121፡1፤ ሉቃ.18፡10-14፡፡

በሐዲስ ኪዳንም የሐዋርያት ተከታዮች የኾኑ መነኮሳት፣ ካህናትና ምእመናን በገዳማት፣ በአድባራት፣ የሰንበት ት/ቤት ተማሪዎች፣ የጽዋ ማኅበርተኞች ስለ ማኅበራቸው ጥንካሬና ከማኅበርተኞቹ መካከል አንዱ ችግር ሲገጥመው የማኅበር ሱባኤ ይያዛል፡፡.

  • የዐዋጅ ሱባዔ

የዐዋጅ ሱባዔ በአገር ላይ ድንገተኛ አደጋ፣ አባር ቸነፈርና ጦርነት ሲነደ እንዲሁም ለማኅበረ ምእመናን አስጊ የሆነ መቅሰፍት ሲከሰት፣ እግዚአብሔር መሽቱን በምሕረት ቁጣውን በትዕግሥት እንዲመልስ የሚያዝ የሱባዔ ዓይነት ነው፡፡ ለዚህ ዓይነቱ ሱባዔ የነነዌ ሰዎችና በፋርስ በስደት ይኖር የነበረ እስራኤላውያን ተጠቃሾች ናቸው፡፡ የነነዌ ሰዎች የዮናስን ስብከት ሰምተው ከሊቅ እስከ ደቂቅ ለሦስት ቀን ከመብል ከመጠጥ ተከልክለው በመጾም በመጸለይ እግዚአብሔር መዓቱን በምሕረት ቁጣውን በትዕግሥት እንዲመልስ አድርገዋል፡፡ ሌላው በፋርስ በስደት ይኖር የነበረ አይሁድ በአስቴር ትእዛዝ የያዙት ሱባዔ ተጠቃሽ ነው፡፡ በዚያን ዘመን አርጤክስስ አይሁድ በያሉበት እንዲገደሉ በማዘዙ ከዚህ የጅምላ ጭፍጨፋ ለመዳን አይሁድ በዐዋጅ ሱባዔ ገብተዋል፡፡ አስቴር ገብታ ንጉሡን ስታናግረው ሌላው ሕዝብ በውጭ ዐዋጅ ዐውጀው ሱባዔ ገብተው ፈጣሪያቸውን ተማፅነዋል፡፡ አስቴር 4፡16 – 28፡፡

በአገራችንም ይህን የመሰለ የዐዋጅ ሱባዔ በዐፄ ምኒልክ ዘመነ መንግሥት ተደርጓል፡፡ ፋሽስት ጣልያን አገራችንን በመውረር ኢትዮጵያን ቅኝ ተገዥ ለማድረግ ድንበሯን አልፎ በመጣበት ወቅት ንጉሠ ነገሥት ምኒልክ፡- «ጉልበት ያለህ በጉልበትህ ጉልበት የሌለህ በጸሎትህ ርዳኝ» በማለት የዐዋጅ ሱባዔ መያዛቸው ይነገራል፡፡ በዚህም መሠረት በየገዳማቱ ምሕላ ተይዟል፤ ንጉሡም ታቦተ ጊዮርጊስን ይዘው ዓለምን እጅግ ያስደነቀ ጥቁሮችን ለነጻነታቸው እንዲነሣሱ የሚያስችል ፋና ወጊ የሆነ ድል አግኝተው አገራችንን ለቅኝ ግዛት ያሰበውን ፋሽስት ጣልያንን ማሸነፋቸው በከፍተኛ ስሜት የምናስታውሰው ነው፡፡

ቅድመ ዝግጅት

ሱባዔ መግባት የሚፈልግ ምእመን ቅድመ ዝግጅት ማድረግ ይኖርበታል፡፡ ያለምንም ዝግጅት ሱባዔ መግባት ለፈተና ያጋልጣል፡፡ ስለዚህ ቅድመ ሱባዔ /ሱባዔ ከመግባት አስቀድሞ/፣ ጊዜ ሱባዔ/ በሱባዔ ጊዜና ድኅረ ሱባዔ /ከሱባዔ በኋላ/ ዝግጅት አስፈላጊ ነው፡፡

ቅድመ ሱባዔ /ሱባዔ ከመግባት አስቀድሞ/

በመጀመሪያ ሱባዔ የምንገባበትን ምክንያት ለይቶ ማወቅ ያስፈልጋል፡፡ አንድ ሰው ሱባዔ የሚገባበትን ዓላማ ለይቶ ካስቀመጠ ከሱባዔ በኋላ የሚጠበቀውን ነገር ማግኘት አለማግኘቱን ይረዳል፡፡ ይህ ሳይሆን ሱባኤ ቢገባ ከሱባኤው በኋላ የጠየቀው ነገር ስለሌለ ትርጉም ያጣል፡፡ ስለዚህ ሱባዔ ከመግባታችን በፊት ለምን ሱባኤ ለመግባት እንዳሰብን ለይተን ማወቅ ይኖርብናል፡፡

ሱባዔ ለመግባት የወሰንበትን ምክንያት ከለየን በኋላ ምክንያታችንን ይዘን የንስሐ አባታችንን ማማከር ያስፈልጋል፡፡ ምክንያቱም በምክረ ካህን መጓዝ መጀመር ክርስቲያናዊ ግዴታ ነው፡፡ ከዚህ ባሻገር በአባትነታቸውና በሕይወት ልምዳቸው ምን ማድረግ እንደሚገባን ምክር ለማግኘት እገዛ ያደርግልናል፡፡ ቅድመ ሱባኤ ከንስሐ አባት ጋር መመካከር ተገቢ ይሆናል፡፡ ለምሳሌ አንድ ሰው በሱባዔ ወቅት የተለያዩ ፈተናዎች ቢያጋጥሙት የተሰጠውን ምክር በመጠቀም ፈተናውን ለመቋቋም ይችላል፡፡ እንዲሁም የንስሐ አባቱ በሱባዔ ወቅት በጸሎት እንዲያስቡት መማከር የራሱ የሆነ ድርሻ አለው፡፡

ሱባዔ ለመግባት ስናስብ ለምን ያህል ቀናት መቆየት እንዳለብን መወሰን ያስፈልጋል፡፡ ሱባዔ ከዚህ እስከዚህ እቆያለሁ ብለን ዕቅድ የምንይዝበት ነው፡፡ እንደ አቅማችንና እንደ ችሎታችን ከዚህ ቀን እስከዚህ ብለን በመወሰን ሱባዔ መግባት ተገቢ ይሆናል፡፡ ለምሳሌ፡- ምንም ዓይነት ልምድ ሳይኖረው አንድ ሰው «በዋሻ እዘጋለሁ» ቢል ከጥቅሙ ጉዳቱ ሊያመዝን ይችላል፡፡ ምክንያቱም በሱባዔ ወቅት ፈተና ስለሚበዛ የሚመጣበትን ፈተና መቋቋም ባለመቻል ሱባዔው ሊቋረጥ ይችላል፡፡ ስለዚህ ቅድመ ሱባዔ ዐቅምንና ችሎታን አገናዝቦ መወሰን ተገቢ ነው፡፡

ሌላው ቅድመ ሱባዔ ለሱባዔ ተስማሚ የሆነ ወቅትና ቦታ መምረጥ ተገቢ ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያን በአብዛኛው ሱባዔ የሚገባው አጽዋማትን ተከትሎ ነው፡፡ ስለዚህ ሱባዔ የምንገባበት ወቅት የጾም ወቅት መሆን አለመሆኑን መለየት ያስፈልጋል፡፡ በአጽዋማት ወቅት የሚያዝ ሱባዔ ለተሐራሚ ጠቀሜታው እጅግ የጐላ ነው፡፡ ምክንያቱም በአጽዋማት ወቅት ብዙ አባቶች ሱባዔ ስለሚይዙ ከአባቶች ጸሎት ጋር ልመናችንና ጸሎታችን ሊያርግ ይችላል፡፡ ስለዚህ ወቅትን ለይቶ ማወቅ ያስፈልጋል፡፡

እዚህ ላይ «ከወርኃ አጽዋማት ውጭ ሱባዔ አይያዝም» የሚል አቋም ለመያዝ አይደለም፡፡ አንድ ሰው ፈተና ከአጋጠመው በማንኛውም ጊዜ ሱባዔ ሊገባ እንደሚችል እዚህ ላይ ለመጠቆም እንወዳለን፡፡ ከዚህም ባሻገር ሱባዔ የምንይዝበትን ቦታ መምረጥ አለብን፡፡ ለሱባዔ የምንመርጣቸው ቦታዎች ለፈተና የሚያጋልጡ መሆናቸውን ማረጋገጥ ያስፈልጋል፡፡ ይኸውም ሱባዔ ከተገባ በኋላ ኅሊናችን እንዳይበተን እገዛ ያደርግ ልናል፡፡ ጫጫታና ግርግር የሚበዛበት ቦታ በሰቂለ ኅሊና ለመጸለይ አያመችም፡፡ ስለዚህ ሱባዔ የምንይዝባቸው ቦታዎች ከከተማ ራቅ ያሉ ገዳማትና አድባራት ተመራጭ ናቸው፡፡

ጊዜ ሱባዔ /በሱባዔ ጊዜ/

በጸሎት ሰዓት ዓምድና ግድግዳ ሳይደገፉ መቋሚያ ሳይዙ በሁለት እግር ቀጥ ብሎ በመቆም መጸለይ ይኖርብናል፡፡ እንዲሁም ፊትን ወደ ምሥራቅ መልሶ መቆም ወዲያና ወዲህ ወደ ግራ ወደ ቀኝ አለመዟዟር በሰፊሐ እድ በሰቂለ ኅሊና ኾኖ መጸለይ ይገባል፡፡ መዝ.5፡3፤ መዝ.133፡2፤ ዮሐ.11፡41፡፡

በሱባዔ ወቅት በቅደም ተከተል መጸለይ አለብን፡፡ መጀመሪያ «በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አአትብ ገጽየ ወኩለንታየ በትእምርተ መስቀልኸ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አንዱ አምላክ መላ ሰውነቴን በትእምርተ መስቀል አማትባለሁ» እያለ ሰጊድን ከሚያነሣው ሲደርስ መስገድ መስቀልን ከሚያነሣ ላይ ስንደርስ ማማተብ ይገባል፡፡

በማስከተል አቡነ ዘበሰማያት፣ መዝሙረ ዳዊት፣ ውዳሴ ማርያምና ሌሎች በመዝገበ ጸሎት የተካተቱትን መጸለይ፤ ቀጥሎ አቡነ ዘበሰማያት፣ ጸሎተ እግዝእትነ ማርያምን፣ ጸሎተ ሃይማኖትን ከጸለይን በኋላ አቡነ ዘበሰማያት መድገም፤ ከዚያ 41 ጊዜ ኪርያላይሶን ይባላል፡፡ ሌላው በሱባዔ ጊዜ ከተሐራሚ የሚጠበቀው ነገር ኃጢአቱን እያሰበ ማዘን ማልቀስ ነው፡፡ ሲያለቅስም ለእያንዳንዱ በደል እንባ ማፍሰስ ያስፈልጋል፡፡

በመጨረሻም ሱባዔ የገባ ሰው ሱባዔውን ሳይጨርስ ወይም ሱባዔውን አቋርጦ ከማንም ሰው ጋር ፈጽሞ መገናኘት የለበትም፡፡

ድኅረ ሱባዔ /ከሱባዔ በኋላ/

ለቀረበ ተማኅፅኖ እግዚአብሔር የሚያደርግልንን ነገር መጠበቅ ይኖርብናል፡፡ እግዚአብሔር ላቀረብንለት ምልጃና ጸሎት እንደ ልባችን መሻት እንደ እርሱ ቸርነት እርሱ በወደደ ጊዜ ያደርግልናል፡፡ ሱባዔ የገባ ሰው ሁሉ ራእይ ላያይ ይችላል፡፡ ምክንያቱም የእግዚአብሔር መልስ አሰጣጥ ለማንም ግልጽ አይደለም፡፡ ከሱባዔ በኋላ መጀመሪያ የምናገኘው የኅሊና ሰላምን ነው፡፡ ይህ ትልቅ የአምላክ ስጦታ ነው፡፡ ከዚህ ባሻገር ሱባዔ ገብተን ያሰብነውን ካላገኘን ዳግመኛ ተዘጋጅተን እስከ መጨረሻው ሰዓት መማፀን መጽናት ይኖርብናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር