ቤተ ክርስቲያንና የፓትርያርክ ምርጫ

ነሐሴ 25 ቀን 2004 ዓ.ም.

በዲ/ን ብርሃኑ አድማስ

ቤተ ክርስቲያን አንዲት፣ ቅድስት፣ ኩላዊትና ሐዋርያዊት መሆኗን ጥንታውያን አብያተ ክርስቲያን ሁሉ ይቀበላሉ፤ በመሠረተ እምነታቸው ውስጥም አካትተው በጸሎትና በአስተምህሮ ይጠቀሙበታል፡፡የዚህ መሠረታዊ ምክንያቱ ደግሞ ከዘመነ ሐዋርያት ጀምሮ ይህ ትምህርት ቢኖርም ነገር ግን መልእክቱን በአግባቡ ካለመረዳት የተነሣ እነ አርዮስና መቅዶንዮስ በትውፊት ከሐዋርያት ጀምሮ የመጣውን የቅዱሳት መጻሕፍት ትርጓሜ መሠረት መቀበልን ቸል ብለው በራሳቸው መንገድ ሔደው ስለሳቱ በጉባኤ ኒቅያ በማያሻማ መንገድ ቤተ ክርስቲያን አንዲት፣ቅድስት፣ ሐዋርያዊት እና ኩላዊት መሆኗን አስቀመጡ፡፡ በኋላ በጉባኤ ቁስጥንጥንያ ደግሞ ሁላችንም እንድንጸልይበት በተዘጋጀው አንቀጸ ሃይማኖት ላይ (ጸሎተ ሃይማኖት) ‹‹ ወነአምን በአሐቲ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንተ ላዕለ ኩሉ ጉባኤ ዘሐዋርያት›› የሚለው የጸሎታችን መፈጸሚያ እንዲሆን ተደነገገ፡፡ በዚህም መሠረት እነዚህን ዓለም አቀፍ ጉባኤያት የሚቀበሉ ሁሉ የሚቀበሉትና የሚመሩበት መሠረታዊ ትምህርተ ሃይማኖት /doctrine/ ሆነ፡፡

ይሁን እንጂ እየዋለና እያደረ ሲሔድ ቃላቱን ተርጉመው የሚረዱበት ሁኔታ እንደገና እየተለያየ መጣ፡፡ ለምሳሌ ያህል ከዚሁ አንቀጸ ሃይማኖት የሚነሱትን ሦስት መሠረታዊ ልዩነቶች ማየት ይቻላል፡፡ የመጀመሪያው ራሱ‹‹ቤተ ክርስቲያን›› የሚለውን ጽንሰ ሀሳብ መረዳት ላይ ያለው ልዩነት ነው፡፡ በፕሮቴስታንቱ ዓለም ቤተ ክርስቲያን በአንድ ቦታ የተሰባበሰቡት ሰዎች ኅብረት ብቻ ነው፡፡ ከዚህ አለፍ የሚሉትም ቢሆን በምድር ያለውን የአማኞቻቸውን ኅብረት አንድ መንጋ እንዲሁም በሰማይ ያሉትን ደግሞ ሁለተኛ መንጋ አድርው በአንድ እረኛ ሁለት መንጋ ሀሳብ የሚያራምዱ እንደ ሆኑ የምዕራባውያን ጽሑፎች ያሳያሉ፡፡ በምሥራቃውን ትውፊት ወይም በኦርቶዶክስ ግን ‹ቤተ ክርስቲያን› ማለት በምድር ያሉት ምእመናንና ተጋድሏቸውን የፈጸሙ ቅዱሳን ኅብረት ወይም አንድነት ናት፡፡ “እንተ በምድር ሥረዊሃ ወበሰማይ አእጹቂሃ..” “ሥሮቿ በምድር ቅርንጫፎቿም በሰማይ ያሉ” የሚለው የቅዱስ ያሬድ ትምህርትም ለዚህ ትልቅ አስረጂ ነው፡፡ በሰማይ ያሉት በዚህ በእንግድነት ከምንኖርበት ምድር ተጋድሏቸውን ፈጽመው ሀገራቸው ገብተው ሽልማታቸውን ተቀብለው በድል ዝማሬ ላይ ያሉ ሲሆን በዚህ ያለነው ደግሞ በዕድሜ ዘመናችን እየተጓዝን ያለንና ገና ተጋድሏችን ያለፈጸምን መሆናችን እሙን ነው፡፡ ሆኖም በምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያንና ብልቶቹ በሆንለት በቤተ ክርስቲያን ራስ በክርስቶስ አንድ ስለሆንን ቤተ ክርስቲያን አንዲት ብቻ ናት፤ መንጋው አንድ እረኛውም አንድ፡፡ ለምሳሌ በእኛም ሆነ በሌሎቹ ኦርቶዶክሶች ያለውን ቅዳሴ በአስተውሎት ብንመረምረው ይህን ዶግማ ፍንትው አድርጎ ያሳየናል፡፡ ወደ ፊት በደንብ የምናየው ቢሆንም ለቤተ ክርስቲያን አስተዳደር መነሻውና መሠረቱ ይህ ነው፡፡

ታዲያ ይህን ‹‹ ቤተ ክርስቲያን አንዲት ናት›› የሚለውን አንቀጹ ራሱ መጽሐፍ ቅዱሳዊ በመሆኑ ሁሉም ቢቀበሉትም በትርጉም ግን ልዩነት ተፈጥሯል፡፡ የሮማ ካቶሊክ ‹አንድነትን›› በሮማው ፓፓ ሥር በመተዳደር ስትተረጉመው ኦርቶዶክሶቹ ግን አንድነት የሚገለጸው ዓለም በሙሉ በአንድ በመተዳደሩ አይደለም፤በምድር ተጋድላቸውን እያደረጉ ያሉ ምእመናንን በአንድ ምድራዊ ሃይማኖታዊ ተቋም አስተዳደርም የአነድነቱ ምንጭ አይደለም፤ ነገር ግን አማናዊ ሥጋውንና ደሙን ስንቀበልና የክርስቶስ ብልቶች ስንሆን ያን ጊዜ በአንዱ በክርስቶስ አንድ እንሆናለን ግንዱ አንድ ስለሆነ በዚያ የወይን ግንድ ያሉ ምእመናን ሁሉ በዚያው ግንድ ላይ በመሆናቸው ወይም አካሉ በመሆናቸው አንድ ናቸው፤ቤተ ክርስቲያንንም አንድ የሚያሰኛት ይህ የአንዱ ክርስቶስ ብልትነታችንንና አንድ አካል መሆናችን ነው ፡፡ “…ይዌልጦሙ በቅጽበት አባላተ ክርስቶስ ይኩኑ፤ በኃይለ ጥበቡ መንክር ወዕጹብ ኪኑ” “ድንቅና ዕፁብ በሆነ በጥበቡ ኀይል የክርስቶስ አካላት ይሆኑ ዘንድ በቅጽበት ይለውጣቸዋል፡፡” እንዳለ የመልክአ ቁርባን ደራሲ፡፡የኦርቶዶክሳውያን ትርጓሜ ይህን መንፈሳዊነትንና ከክርስቶስ ጋር ያለንን ውሕደት መሠረት ያደረገ ነው፡፡

 

ከዚሁ ጋር በትልቁ መሠረት የሚሆነው ደግሞ ‹‹ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊት ናት›› የሚለው እምነት ነው፡፡ እዚህም ላይ ትልቅ ልዩነቶች አሉ፡፡ ቤተ ክርስቲያን ሐዋርዊት ናት የምትባለው መቼ ነው የሚለውን ጥያቄ ሲመልሱ ኦርቶዶክሳዊያን ሦስት ነገሮች ሲሟሉ ነው ይላሉ፡፡ የመጀመሪያው ሢመተ ጵጵስና ወፓትርያርክን የሚመለከት ነው፡፡ ይህም አንዲት ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊት የምትባለው ጌታ ከሾማቸው ከሐዋርያት አንሥቶ ያልተቋረጠ ክትትል ያለው የሢመት ሐረግ ሲኖር ነው፡፡ ለምሳሌ የእኛ ከቅዱስ ማርቆስ ወንጌላዊ አንሥቶ ሳይቋረጥ እስከ ቄርሎስ ስድሰተኛ (116ኛው) ፓትርያርክ ከደረስ በኋላ ለእኛ 117ኛ ሆነው አባ ባስልዮስ ኢትዮጵያዊ ተሾሙ፡፡ አሁን 121ኛው አባ ጳውሎስ ሆኑ ማለት ነው፡፡ ሁለተኛው ቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊት የሚያሰኘው ደግሞ ሐዋርያዊ ትዉፊትን ተቀብላ የምትተገብር መሆኗ ነው፡፡ ከእነዚህም አንዱ ጳጳሳትን በተለይም ፓትርያርኮችን የምትመርጥበት ሐዋርያዊ ትዉፊት ወሳኙ ነው፡፡ ሦስተኛው ቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ የሚያሰኛት ደግሞ ሐዋርያዊ ክትትሉን የጠበቀ የቅዱሳት መጻሕፍት ትርጓሜ ነው፡፡ ዶግማ የሚባለውም የዚህ ትርጓሜ ውጤት ነው፡፡

 

ከእነዚህ ነጥቦች ተነሥተን የእኛን ቤተ ክርስቲያን ሂደት (Experiance) መዳሰስ ቅድሚያ የሚሰጠው ሆኖ ይገኛል፡፡ ምክንያቱም አንደኛ በታሪካችን ውስጥ ከነበሩት ጠንካራ ጎኖች ብቻ ሳይሆን ከድከመቶቹም የምንወስዳቸውን ጥቅሞች በቅርበት ለመመርመር፤ ሁለተኛም ከዚያ ተነሥተን ወደፊት የምንሔድበትን ለማየት ስለሚጠቅም ነው፡፡

 

ቀደም ብለን እንደገለጽነው የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊት የምትባለው ቅዱስ ማርቆስ ወንጌላዊ ሲመተ እድ ባለተቋረጠና ክትትል ባለው ሐዋርያዊ ክህነት (Apostolic succession)እስካሁን በመኖሯና ሐዋርያዊ ትውፊትንም ከዚያው ሳትወጣ የምትፈጽም በመሆኗ ነው፡፡ ሆኖም በታሪካችን ሐዋርያዊ ትውፊትና ቀኖና የተፈተኑበት ጊዜ አልነበረም ማለት አይደለም፡፡ ከሁለት ሺሕ ዓመት አገልግሎት አንጻር ሲታይ አጋጣሚዎች ጥቂትና ጊዜዎቹም አጫጭር ቢሆኑም ከትፊዉቱ የመውጣትና የውጤቱንም መከራና ፈተና ማጨድ እንደነበረ ግን ታሪካችን ያስረዳል፡፡ ምንም እንኳ ዘመኑ ትንሽ ዕድሎቹም ጥቂት የነበሩ ቢሆኑም ያስከተሉት ጥፋትና ጉድለት ግን ትንሽ አልነበረም፡፡ሆኖም በየዘመኑ የነበሩ አባቶች ከችግሮቹ እየተማሩ ትውፊታቸውን አጥብቆ ወደመጠበቅ በመመለስ ከችግራቸው ወጥተዋል፡፡ ለመሆኑ ቀኖናውና ትውፊቱ ምንድን ነው?

 

ትውፊቱ

የቤተ ክርስቲያንን የጵጵስናና የፕትርክና ሹመት ታሪክ ጸሐፊዎች መነሻ የሚያደርጉት ጌታችን ሐዋርያትን የመረጠበትን ሁኔታና በሐዋርያት ሥራ ላይ የተገለጸውን የማትያስን ምርጫ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያንን ‹‹ ሐዋርያዊት›› በሚያሰኟት በእነዚህ ሁለት የምርጫ ክስተት ውስጥ ሦስት መሠረታዊ መስፈርቶችን እንደ ምሳሌ ይወስዳሉ፡፡ እነዚህም

 

1ኛ) የሐዋርያት ከተርታው ሰው ውስጥ መመረጣቸው

ታሪክ ጸሐፊዎቹ እንደሚሉት ሁሉን ማድረግ የሚቻለው ጌታ ከምሁራነ ኦሪት ቅኖቹን መምረጥና ማብቃት መለወጥ እየተቻለው እነርሱን ትቶ ከተርታ ሰዎች ምንም ካልተማሩትና ምንም ልምድም ሆነ ዕውቀት የሌላቸውን መርጦና አምጥቶ አስተምሮ ቅዱሳን ሐዋርያትን የሾመው ወደ ፊት ፓትርያርኮች ከአነሥተኛው መዓርግ እየተመረጡ እንዲሾሙ ሲያሰተምረን ነው ይላሉ፡፡ እንዲያውም እንደ ቅዱስ ጳውሎስና እንደ አጵሎስ ያሉትን ምሁራነ አሪት እንደሚመልሳቸው እያወቀና ክብራቸውንም በተለይ ቅዱስ ጳውሎስ ቁጥሩም መዓርጉም ከሐዋርያት ሆኖ ሳለ መጀመሪያ ያልተመረጠው ምርጫው መንፈሳዊነትን እንጂ ዕውቀትን መሠረት ያደረገ እንዳይሆን ሥርዓት ሲሠራልን ነው በማለት ያስረግጣሉ፡፡ ጌታ ሐዋርያትን ከመረጠ በኋላ ግን አስተምሯቸዋል፤ በዚህም መሠረት የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት በተገቢው መንገድ ለአገልግሎትና ለምሥጢራት በሚያስችል ሁኔታ ከተማረና በርግጥ መንፈሳዊ ሆኖ ቀኖና ቤተ ክርስቲያን ጠብቆ ከተመረጠ ሌላውን ዕውቀት ከራሱ ከጌታ ሊያገኘው ይችላል ባዮች ናቸው፡፡

2ኛ)የሰዎች ድርሻ

በቅዱስ ማትያስ ምርጫ ሒደት ውስጥ ከተገኙት ሁለት መሠራታዊ ትውፊቶች አንዱ ደግሞ ሐዋርያት መጀመሪያ ሁለት ሰዎችን መርጠው ድርሻቸውን መወጣታቸው ነው፡፡ ስለዚህ አባቶችን በመምረጥ ሒደት ሓላፊነት ያለባቸው አካላት አሉ፡፡ እነዚህ አካላት ግን ልክ እንደ ሐዋርያት ሊሾም ከታሰበው በላይ ቁጥር ያላቸውን መርጠው ማቅረብ አለባቸው፡፡ ሐዋርያት አንድ ሰው በይሁዳ ለመተካት ሲፈልጉ ሁለት እንዳቀረቡት ሁሉ ለመጨረሻው አባትነት ለፓትርያርክም አባቶች መምረጥ ያለባቸው ከአንድ በላይ መሆን አለበት፡፡

3ኛ) የእግዚአብሔር ምርጫ

ቅዱሳን ሐዋርያት ማትያስንና በርናባስን (ዮሴፍን) ከመረጡ በኋላ ከሁለቱ አንዱን የመምረጡ ድርሻ ግን የእግዚአብሔር ነበረ፡፡ ስለዚህ ማንኛችንም ቢሆን ከሐዋርያት ልንበቃ አንችልምና በወደደው መንገድ የእግዚአብሔርን የመምረጥ ዕድል የሰጠ መሆን አለበት፡፡የጥንታዊቷ ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ትውፊትም በእነዚህ መሠረቶች ላይ የተገነባ የሰውንና የእግዚአብሔርን ድርሻ በግልጽ የሚያስቀምጥ ነበር ይላሉ፡፡

ቀኖናውስ?

‹‹የእግዚአብሔርን መንጋ በእውቀት ለመጠበቅ ፍጹም የሆነ የሰው እጥረት አለ፡፡… ትክክለኛ የቀኖና እውቀትም የለም፡፡ ኃጢአትን ለመሥራት ሙሉ ነጻነት አለ፡፡ ሰዎች በአማላጅ ክህነትና እልቅና በተሾሙ ጊዜ ውልታቸውን ለመመለስ ሲሉ ቀኖናዊ ጥፋቶችን ቸለል ይላሉ፡፡›› ባስልዮስ ዘቂሳርያ /Basil of Caesaria, To the Italians and Gauls, letter 92/

“አንድ ጳጳስ በድርቅና በረሃብ፣ በተሾመባት ከተማ ትንሽ መሆን፣ በሕዝቡ ማነስ፣ በቂ ገቢ በሀገረስብከቱ ባለመኖሩና በመሳሰሉት ምክንያት ከተሾመባት ከተማ ወይም መንደር ተነሥቶ ወደ ሌላ አይሂድ፤ ከዚህ የተሻለ ይሰጠኝ ብሎም አይጠይቅ፤ እያንዳንዱ ከእግዚአብሔር የሚከፈለው ዋጋ አለውና” ይላል፡፡ በዚህ መሠረት

1ኛ) አንድ (ሊቀ) ጳጳስ ወደ ፕትርክና ቢመጣ እንደሚስት የምትቆጠርለትን ሀገረ ስብከቱን በማቅለሉና ሌላ የተሻለች መንበር (ሚስት) በመፈለጉ ምክንያት ብቻ የተነቀፈ ነው፡፡

2ኛ) ለፕትርክና ሲሾምም ጳጳሳቱ እጃቸውን የሚጭኑበት ‹‹ በ…ሀገር እና…ከተማ›› ብለው ስለሆነ ሁለተኛ እንደ ማግባት ተቆጥሮ እንደ ዝሙት ያስቀጣዋል ወይንም ክህነቱን ያሳጣዋል ይላሉ፡፡

3ኛ) ጌታ እንዳደረገው ወደ ላይኛው ሥልጣን የሚመጡት ከታችኛው ከአበ ምኔትነትና በታች ካለው እንደሆነ ትውፊቱ ያስገድዳልና፡፡

ይህንን ሀሳብ በትክክል ለመረዳት ግን የፓትርያርክን መሠረተ ሀሳብ በደንብ መፈተሽና በትክክለኛው ሁኔታ መረዳት ያስፈልጋል፡፡ ምክንያቱም በሐዋርያት ትውፊት መሠረት ፓትርያርክ ወይንም ፖፕ የሚለው ቃል ራሱ ለመጀመሪያ ጊዜ ጥቅም ላይ የዋለው ከ232-247 ዓ.ም. ድረስ በእስክንድርያ መንበር በተሾመው በአባ ሔራክልዮስ ዘመን ነው፡፡ ይህም ማለት ፓትርያርክነት በክህነት መዓርግ ብልጫ የለውም ማለት ነው፡፡ ልክ በዲያቆንና በሊቀ ዲያቆን ወይም በጳጳስና በሊቀ ጳጳስ ወይም ደግሞ በቄስና በቆሞስ መካከል የሥልጣነ ክህነት ልዩነት እንደሌለው ሁሉ በጳጳስና በፓትርያርክም መካከል የሥልጣነ ክህነት መበላለጥ የለም፡፡ ይህም ማለት ዲያቆንን ሊቀ ዲያቆን በማድረግ ሒደት ድጋሚ የዲቁና ሥልጣን እንደማይሰጠው ሁሉ ወይም ድጋሚ ክህነት ቢሰጠው ውግዘት ያለበት እንደሆነው ሁሉ በፕትርክና ጊዜም የሚሰጠው ክህነት የጵጵስና ከሆነ ድጋሜ ክህነት ተሰጠው ስለሚያሰኝና በሁለተኛ ሀገረ ስብከትም ተሾመ የሚለውን ትርጉም የሚያመጣው ምሥጢር ይህ ስለሆነ ነው ጳጳስ ሀገረ ስብከቱን ትቶ ፓትርያርክ እንዳይሆን ቀኖናው የሚከለክለው፡፡ ይህ ከሆነ ፓትርያርክ ማለት የትክክል የበላይ ( Father among equals) ነው እንጂ የጳጳሳት ሁሉ ፍጹም የበላይ( father above equals) አይደለም፡፡ እንግዲህ ግብጾች እየጠበቁት ነው የሚባለው ይህ ነው፡፡

ሙሉውን እዚህ በመጫን ያንብቡ

 

አሥረኛው ጠቅላላ ጉባኤ ተራዘመ

ነሐሴ 24 ቀን 2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደጀኔ

ከነሐሴ 26-28 ቀን 2004 ዓ.ም. ሊካሄድ የነበረው የማኅበረ ቅዱሳን አሥረኛ ጠቅላላ ጉባኤ ወደ ነሐሴ 30 ቀን 2004 ዓ.ም. ተራዘመ፡፡

 

በኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ክቡር አቶ መለስ ዜናዊ ኅልፈተ ሕይወት ምክንያት ብሔራዊ የሃዘን ቀን በመሆኑ ጉባኤው እንዲራዘም መደረጉን የጠቅላላ ጉባኤው አዘጋጅ አብይ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ የሺዋስ ማሞ ገልጸዋል፡፡

 

ዘንድሮ የሚካሄደው ጠቅላላ ጉባኤ 1 ሺህ ተሳታፊዎች የሚታደሙበት ሲሆን ለቀጣዩ 4 ዓመታት ማኅበሩን የሚመራ አዲስ አመራር እንደሚመረጥም አቶ የሺዋስ ማሞ ጨምረው ገልጸዋል፡፡

 

ጠቅላላ ጉባኤው እስከ ጳጉሜ 2 ቀን 2004 ዓ.ም. ይቀጥላል፡፡

abuneteklhymanote

ሐዲስ ሐዋርያ ተክለ ሃይማኖት

ነሐሴ 23 ቀን 2004 ዓ.ም.


abuneteklhymanoteጻድቃንን ማሰብ ሥራቸውን መዘከር ክርስቲያናዊ ሕይወታችንን ያጐለምሳል፡፡ የበረከታቸው ተሳታፊ በማድረግ በነፍስ በሥጋ የሚታደገንን የሚረባን፤ የሚጠቅመን ይሆናል፡፡ ስለጻድቁ አባታችን ስለ ቅዱስ ተክለ ሃይማኖትም የምናስበው ከዚህ የተለየ አይደለም፡፡ በመንፈሳዊ አርአያነታቸው፣ በጸሎታቸውና በትምህርታቸው ከከበቡን የነፍስ ጠላቶች፤ ከርኲሳን መናፍስትና ከጨለማው ልጆች፣ ከክፉ ሰዎች ሽንገላና ተንኰል ለመሰወርና ለመጠበቅ ከእግዚአብሔር የተቀበሉት ሥልጣን ምን ጊዜም ይሠራል፡፡ በጻድቃን መኖር ሀገር ከጥፋት ትድናለች፡፡ የጻድቃንን ስም ጠርቶ እግዚአብሔርን በመለመን በረከትና ረድኤት ይገኛል፡፡ ስለጻድቃን ብሎ እግዚአብሔርም ምሕረቱን ያድላል፡፡ ስለዚህ ነው ቤተ ክርስቲያናችን ጻድቃንን እንድናስባቸው፣ በስማቸውም ለድሆችና ለጦም አዳሮች እንድንመጸውት መታሰቢያቸውን እንድናደርግ የምትመክረን፤ የምታስተምረን፡ ጻድቁ ተክለ ሃይማኖትንም የምናስባቸው ከዚሁ የቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ በመነሣት ነው፡፡ ማቴ.10፥41-42 ጻድቃንን በሕይወተ ሥጋ ሳሉም ቢሆን፤ ከሞቱም በኋላ በአጸደ ነፍስ በጸሎታቸው ለሚታመኑ፣ በቃል ኪዳናቸው ለሚማጸኑ፣ የድኅነተ ሥጋ፣ የድኅነት ነፍስ ምክንያት ናቸው፡፡

በዚህ መሠረት ከቅዱሳን አባቶች መካከል ለኢትዮጵያ ሐዲስ ሐዋርያ ሆነው የተመረጡና ከጻድቃን መካከል የሆኑትን የቅዱስ ተክለሃይማኖት በዓለ ዕረፍትን መታሰቢያ ምክንያት በማድረግ ዜና ሕይወታቸውን ከዚህ እንደሚከተለው በአጭሩ እናቀርባለን፡፡

 

ጻድቁ አባታችን ተክለ ሃይማኖት በአምላክ ፈቃድ፣ በሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ብሥራት፤ ከአባታቸው ከካህኑ ጸጋ ዘአብና ከእናታቸው ከቅድስት እግዚእ ኀረያ ታኅሣም 24 ቀን 1212 ዓ.ም.  ተወለዱ፡፡ ወላጆቻቸው ስማቸውን ፍሥሐ ጽዮን በማለት አወጡላቸው፡፡ በተወለዱ በሦስተኛውም ቀን እሑድ ከጠዋቱ ሦስት ሰዓት ከእናታቸው ዕቅፍ ወርደው “አሐዱ አብ ቅዱስ፤ አሐዱ ወልድ ቅዱስ፤ አሐዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ፡- አንዱ አብ ቅዱስ ነው፤ አንዱ ወልድ ቅዱስ ነው፤ አንዱ መንፈስ ቅዱስ ቅዱስ ነው፡፡” በማለት የሥላሴን ስም ጠርተው አመስግነዋል፡፡ በተወለዱ በ15 ዓመት ዕድሜያቸው ዲቊናን፣ በ22 ዓመታቸው ቅስናን ከግብፃዊው ጳጳስ ከአባ ጌርሎስ /ቄርሎስ/ ተቀብለዋል፡፡

 

ከዕለታት በአንዱ ቀን አባታችን ወደ ጫካ ለአደን ሄደው ሳለ፤ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ግሩም ድንቅ የሆነ ልብስ ለብሶ ታያቸው፡፡ አባታችንም እንደዚህ ባለ ገናንነት የማይህ ጌታዬ ማነህ?” አሉት፡፡ ቅዱስ ሚካኤልም “ዘወትር የምጠብቅህ ካንተ የማልለይ እናትህንና አባትህንም ስላንተ ከውኃ ስጥመትና ከምርኮ ያዳንኳቸው እኔ ሚካኤል ነኝ፡፡ እንግዲህ አውሬ አዳኝ አትሁን፤ ሰውን ወደ እግዚአብሔር ለመመለስ ሰውን በትምህርት የምታድን ሁን እንጂ፡፡ እነሆ እግዚአብሔር ጽኑዕ ሥልጣን ሰጥቶሀልና፤ ሙት ታስነሣለህ፤ ድውያንን ትፈውሳለህ፤ አጋንንትም አንተን በመፍራት ይሸሻሉ፡፡ ስምህ ፍሥሐ ጽዮን አይሁን፤ ተክለ ሃይማኖት ይሁን እንጂ፡፡ ትርጓሜውም ተክለ አብ፥ ተክለ ወልድ፥ ተክለ መንፈስ ቅዱስ ማለት ነው፡፡” አላቸው፡፡ ቅዱስ ሚካኤል ይህን ሲያነጋግራቸው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሥጋ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር እንደነበር ሆኖ መልከ መልካም ጎልማሳ መስሎ ታያቸው፡፡ ጌታችንም “ወዳጄ እንዴት ሰነበትክ! ቸር አለህን፤” አላቸው፡፡ ብፁዕ ተክለ ሃይማኖትም “ጌታዬ ሆይ አንተ ማነህ? ብለው ጠየቁ፡፡ ጌታም “እኔ የዓለም መድኀኒት ኢየሱስ ነኝ፤ በናትህ ማኅፀን ፈጥሬህ ያከበርኩህ እኔ ነኝ፡፡ በተወለድክ በሦስተኛው ቀን አሐዱ አብ ቅዱስ፥ አሐዱ ወልድ ቅዱስ፥አሐዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ፥ብለህ ታመሰግነኝ ዘንድ የምስጋና ሀብት ያሳደርኩብህ እኔ ነኝ፡፡ በረሃብ ዘመን በቤት የሚያሻው ምግብ ሁሉ ቅቤው፣ የስንዴው ዶቄት በእናት በአባትህ ቤት ይመላ ዘንድ በእጅህ ሀብተ በረከት ያሳደርኩብህ እኔ ነኝ፡፡ ያንን ሰው አንተን በተጣላ ጊዜ በነፋስ አውታር የሰቀለኩት በመዓት ጨንገር የገረፍኩት እኔ ነኝ፡፡ ውኃ ጠምቶህ በለመንከኝ ጊዜ ከደረቅ መሬት የጣፈጠ ውኃ ያመነጨሁልህ አኔ ነኝ፡፡ ከልጅነትህ ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ ብዙ ተአምራት እያደረግሁ በአንተ እጅ የታመሙትን ያዳንኳቸው እኔ ነኝ፡፡ ወደ ፊትም አደርግልሃለሁ፡፡ ይህንን ብሎ ንጹሓት ክቡራት በሆኑ እጆቹ ባረካቸው “ንሣእ መንፈስ ቅዱስ” ብሎ የሹመትን ሀብት አሳደረባቸው፡፡ በምድር ያሰርከው በሰማይ የታሰረ ይሁን፡፡ በምድርም የፈታኸው በሰማይ የተፈታ ይሁን፤ አንተን የሰማ እኔን መስማቱ ነው፤ የላከኝ አባቴንም መስማቱ ነው፡፡ አንተን እንቢ ያለ እኔን እንቢ ማለቱ ነው፡፡ የላከኝ አባቴንም እንቢ ማለቱ ነው፡፡ ይህን ሥልጣን ቀድሞ ለሐዋርያት ሰጥቻቸው ነበር፡፡ ከሐዋርያትም ሹመትን የተቀበለ ጳጳሱ ትሾምና ትሽር ትተክልና ትነቅል ዘንድ ሥልጣንን ሰጠህ፡፡ ይህንንም ያደረኩልህ የጳጳሱን ቃል በመናቅ አይደለም፡፡ የፍቅሬን ጽናት ባንተ እገልጽ ዘንድ ነው እንጂ፡፡ ሐዋርያት ወደአልደረሱበት ሕዝብ በመምህርነት እልክህ ዘንድ በሚካኤል ቃል አዲስ ስም አወጣሁልህ፡፡ አንተም በማናቸውም ሥራ ከነሱ አታንስም፡፡ ሐዲስ ሐዋርያ አድርጌሃለሁና፡፡ ሰውን ሁሉ በእኔ ስም እያስተማርክ ታሳምን ዘንድ፤ ሚካኤልም ባሰብከው ሥራ ሁሉ ረዳት ይሁንልህ፡፡ ሁል ጊዜ ካንተ አይለይም፡፡ በምትሄድበትም ጎዳና ሁሉ እርሱ መሪ ይሁንህ፡፡ እኔም ባለ ዘመንህ ሁሉ አልለይህም” ብሎ ሰላምታ ሰጥቷቸው ዐረገ፡፡ ብፁዕ አባታችንም እጅ ነስተው “ለእኔ ለኀጥኡ የማይገባኝ ሲሆን ይህን ሁሉ ጸጋ የጠኸኝ ስምህ በሰማይ በምድር የተመሰገነ ይሁን” አሉ፡፡ ከዚያች ቀን ጀምሮ ሀብተ ኀይልን የተመሉ ሆኑ፡፡ ከዚያም ወደቤታቸው ተመልሰው ያላቸውን ንብረት ሁሉ ለቤተ ክርስቲያንና ለነዳያን ሰጥተው ጨረሱ፡፡ ከዚያም “አቤቱ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! የመንግሥተ ሰማያትን በር ትከፍትልኝ ዘንድ እነሆ ቤቴን እንደተከፈተ ተውኩልህ” ብለው ቤታቸውን እንደተከፈተ ትተው ወንጌልን ለማስተማር ፈጥነው ወጡ፡፡ /ገድለ ተክለሃይማኖት ዘሠሉስ ምዕ.28 ገጽ 116/

 

ከ1219-1222 ዓ.ም. በከተታ ሦስት ዓመት፣ ወንጌልን አስተማሩ፡፡ ቀጥለውም ዘጠኝ ወር በዊፋት አገልግሎታቸውን ፈጽመዋል፡፡ ከ1223-1234 ዓ.ም. ዳሞት በተባለው ስፍራ ወይም በወላይታ ሀገር ለ12 ዓመታት ከአምልኮተ ጣዖት ወደ አምልኮተ እግዚአብሔር፤ ከገቢረ ኀጢአት ወደ ገቢረ ጽድቅ ትምህርት በመስጠት ተአምራት አድርገው፤ መልሰዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያንንም አንፀዋል፡፡ በዚህ ሀገር ዲያብሎስ በዛፍ ላይ አድሮ አምላክ ነኝ እያለ ለረጅም ዘመናት ሕዝቡን በማሳት የሚጠቀምበትን ዛፍ በተአምራት ከሦሩ ነቅለው አፍልሰዋል፡፡

 

በዚህ ተግባራቸው ጌታችን በቅዱስ ወንጌል “የሰናፍጭ ቅንጣት የሚያህል እምነት ቢኖራችሁ፤ ይሄንን ሾላ ተነቅለህ ወደ ባሕር ተተከል ብትሉት ይታዘዝላችኋል፡፡” ሉቃ.17፥6 ያለውን አምላካዊ ቃል በተግባር አስመስክረዋል፡፡ ከዚህም በኋላ በእግዚአብሔር ፈቃድና ትእዛዝ ወደ አማራ ሳይንት ወሎ በመሄድ ሥርዓተ ምንኲስናን ከአባ በጸሎተ ሚካኤል ገዳም ገብተው ከ1234-1244 ዓ.ም. ለዓሥር ዓመታት የእርድና ሥራ በመሥራትና ገቢረ ታምራትን በማሳየት ጌታ በቅዱስ ወንጌል “ማንም ከእናንተ ታላቅ ሊሆን የሚወድ ለእናንተ አገልጋይ ይሁን፤ ከእናንተ ማንም ፊተኛ ሊሆን የሚወድ የእናንተ ባሪያ ይሁን፡፡ እንዲሁም የሰው ልጅ /ወልደ እጓለ እመሕያው ክርስቶስ/ ሊያገለግል ነፍሱንም ለብዙዎች ቤዛ ሊሰጥ እንጂ እንዲያገለግሉት አልመጣም፡፡ ማቴ.20፥26-28 ያለውን መለኮታዊ ትእዛዝ በተግባር አሳይቷል፡፡ ከ1244-1254 ዓ.ም. አባ ኢየሱስ ሞዓ ወደሚገኙበት ገዳም ሐይቅ እስጢፋኖስ በቅዱስ ሚካኤል መሪነት ሐይቁን በእግራቸው እንደ ደረቅ መሬት በመርገጥ ወደ ደሴቲቱ በመግባት የምንኲስናን ተግባራቸውን በመቀጠል በግብረ ሐዋርያትና በወንጌል የተነገረውን የእርድናን ተግባር ፤የአገልግሎትና ትሩፋት/ሥራ ከፍጻሜ አድርሰዋል፡፡ በአባ ኢየሱስ ሞዓ እጅም የንጽሕና ምልክት የሆነውን የምንኲስናን ቀሚስ ተቀብለዋል፡፡

 

ከ1254-1266 ዓ.ም. ለዐሥራ ሁለት ዓመታት አቡነ አረጋዊ ወዳቀኑት ገዳም በትግራይ ሀገረ ስብከት ወደሚገኘው ደብረ ዳሞ ገዳም በመግባትDebre libanos Monastary. በጊዜው ከነበሩት አበምኔት ከአባ ዮሐኒ ቆብና አስኬማ ተቀብለው በገድል በትሩፋት መንፈሳዊ ተጋድሎአቸውን ቀጠሉ፡፡ ከደብረ ዳሞ ገዳም ወደሌላ ለመሄድ ሲነሡ፤ ክቡር አባታችን ተክለሃይማኖት አበምኔቱና መነኰሳቱ ሲሸኟቸው ሳለ፤ አርባ ክንድ ርዝመት ባለው ገመድ ገደሉን ለመውረድ እንደጀመሩ፤ ገመዱ ከካስማው ሥራ በመቆረጡ እንዳይወድቁ በተሰጣቸው ስድስት የብርሃን ክንፎች እየበረሩ፤ ክንፎቻቸውን እያማቱ ሦስት ምዕራፍ ሄደው ዐርፈዋል፡፡ ከዚያም ወደ ገዳመ ዋሊ ገብተዋል፡፡ በዚህም ጊዜ ነቢዩ ኢሳይያስ የተናገረው ትንቢት “ለደካማ ኀይልን ይሰጣል፤ ጉልበት ለሌለው ብርታትን ይጨምራል፡፡ ብላቴኖች ይደክማሉ፤ ይታክቱማል፡፡ ጐበዛዝትም ፈጽመው ይወድቃሉ፡፡ እግዚአብሔርን በመተማመን የሚጠብቁ ግን ኀይላቸውን ያድሳሉ፤ እንደ ንስርም በክንፍ ይወጣሉ፤ ይሮጣሉ፤ አይታክቱም፡፡ “ኢሳይያስ 40፥29-31 ያለው ቃል በጻድቁ በቅዱስ ተክለ ሃይማኖት ሕይወት ሊተረጐም ችሏል፡፡ ከ1266-1267 ዓ.ም. አንድ ዓመት ሙሉ ገዳማተ ትግራይን በመጐብኘት ኢየሩሳሌምንና ግብፅ ያሉ ቅዱሳት መካናትን ሲጎበኙ ቆይተዋል፡፡ ከዚህ በኋላ አንድ ወር ሙሉ “ዳዳ” በተባለ ስፍራ ይመለክ የነበረውን 75 ክንድ ዘንዶ በጸሎት ኀይል በተአምራት ገድለውታል፡፡ አርባዓቱ እንስሳ /በኪሩቤልና በሱራፌል/ ስም ቤተ ክርስቲያን አንፀው፤ ታቦተ ሕግ /ጽላተ ሕግ/ አስገብተዋል፡፡ ከሴቶችና ከልጆች ሌላ፤ ሦስት ሺህ በጣዖት የሚያመልኩ ወንዶችን መልሰው፤ አጥምቀው አቊርበዋል፡፡ በዚህም ተግባራቸው መድኀኒታችን “እነሆ እባቡንና ጊንጡን ትረግጡ ዘንድ በጠላትም ኀይል ሁሉ ላይ ሥልጣን ሰጥቻችኋለሁ፥ የሚጎዳችሁም ምንም የለም” ሉቃስ 10፥19 ያለው ቃል ተፈጽሞላቸዋል፡፡ ክቡር ዳዊት በመዝሙር 90፥13-14 “በተኲላና በእባብ ላይ ትጫማለህ፤ አንበሳውና ዘንዶውን ትረግጣለህ፡፡ በእኔ ተማምኗልና አስጥለዋለሁ፤ ስሜንም ዐውቋልና እጋርደዋለሁ፡፡” የተባለው ትንቢት ተፈጽሞላቸዋል፡፡ ከ1267-1289 ዓ.ም. በደብረ ሊባኖስ ካለችው ገዳመ አስቦ ዋሻ በመግባት፤ ስምንት ጦሮችን /ሁለቱን በፊት፣ ሁለቱን በኋላ ሁለቱን በቀኝ፣ ሁለቱን በግራ አስተክለው  እጆቻቸውን በትእምርተ መስቀል በመዘርጋት የክርስቶስን ሕማምና ሞት፣ ነገረ መስቀልን በማሰብ በተመስጦ ሌትና ቀን ያለማቋረጥ በጾምና በጸሎት በአርምሞ ተወስነው ሲጋደሉ፤ ከቊመት ብዛት የተነሣ ጥር 4 ቀን 1289 ዓ.ም. አንዲቱ የእግራቸው አገዳ ተሰብራለች፡፡ ደቀ መዛሙርቱም የመንፈሳዊ አባታቸውን ስባረ ዐፅም አክብረው በሥርዓት አኑረውታል፡፡ እግራቸው እስኪሰበር የቆዩባቸው ዓመታት በቊጥር ሃያ ሁለት ናቸው፡፡ በመዓልትና በሌሊት በትጋትና በቊመት በተጋድሎ ብዛት፤ አንዲት የአገዳ እግራቸው ስትሰበር፤ ዕድሜያቸው 92 ዓመት ሆኗቸው ነበር፡፡

 

ከ1289-1296 ዓ.ም. ለሰባት ዓመታት በአንድ እግራቸው በመቆም ያለምግብና ያለውኃ በትኅርምት ሌትና ቀን እንቅልፍ በዓይናቸው ሳይዞር እንደ ምሰሶ ጸንተው፤ በተመስጦ በትጋት ለሰው ዘር ሁሉ ድኅነትን ሲለምኑ ኖረዋል፡፡ ከሰባቱ ዓመታት ውስጥ ጥቂት ውኃ የቀመሱት በአራተኛው ዓመት ብቻ ነበር፡፡ ማቴ.4፥4 የሐ.14፥22፣ 2ቆሮ.11፥26፤ በዚህ ጊዜ ውስጥ ጌታችን ተገልጾ፤ “በሰው እጅ የማይለካውን ይህንን የመንግሥት አዳራሽ ውሰድ” በማለት የመለኮትን ነገር የሚናገር የእሳት አንደበት ያላቸው የመንግሥት ልብስ አልብሷቸዋል፡፡ በመስቀል ምልክት የተጌጡት ሰባት የሕይወት አክሊላት “ስለ ቀናች ሃይማኖትህ፤ ሃይማኖትን ለማስተማር መላዋን ኢትዮጵያን ስለመዞርህ፤ ከአረማውያን ሕዝብ ጋር በሃይማኖት ስትታገል ደምህን ስለማፍሰስህ፤ ወደ ኢየሩሳሌም ወርደህ ልዩ ልዩ የቅዱሳን ቦታዎች ስለመሳለምህ፤ በሰባት ዓመታት ቊመት የአንዱ አገዳ እግርህ ስለመሰበሩ፤ ስለብዙ ጾም ጸሎትህ ስግደትህ፤ ስለልብህ ንጽሕናና ቅድስና” ብሎ አቀዳጅቷቸዋል፡፡ ዝክራቸውን በማዘከር መታሰቢያቸውን የሚያደርጉ ሁሉ በዚህ ዓለምም ሆነ በወዲያኛው ፍጹም ዋጋና ፍጹም ክብር እንደሚሰጣቸው ጌታ ቃል ኪዳን ገብቶላቸዋል፡፡ ያዕ.1፥12፣ ራእ.14፥1213፣ 2ጢሞ.4፥6-8 በመጨረሻም ለዐሥር ቀናት በሕመም ቆይተው፤ ፈጣሪያቸው የገባላቸውን ቃል ኪዳን ለመነኰሳት መንፈሳውያን ልጆቻቸውና ለደቀ መዛሙርቶቻቸው ከነገሩ በኋላ ነሐሴ 24 ቀን በክብር ዐርፈዋል፡፡ በከበረች ዕረፍታቸው ከዚህ የሚከተለውን የሃይማኖት ኑዛዜ አውርሰውናል፡፡

 

“ልጆቼ! አታልቅሱ፤ ነገር ግን የሽማግሌውን የአባታችሁን ቃል ስሙ፡፡ መጀመሪያ እምነታችሁ በእግዚአብሔር ላይ ይሁን፡፡ በዚህ ዓለም እንደተያዙ እንደ ዓለም ሰዎች ስለ ልብስና ስለምግብ አሳብ አታብዙ፡፡ በየጊዜው ሁሉ መጸለይን አታቋርጡ ለቤተ ክርስቲያንም ሌትና ቀን አገልግሉ፡፡ እግዚአብሔር በሚወደው ገንዘብ ንጽሐ ሥጋንና ጾምን ውደዱ፡፡ ውዳሴ ከንቱም የሚቀረውንም የዚህን ዓለም ክብር አትውደዱት፤ እናንተስ የቀደሙትን አባቶች በመከራና በድካም ብዛት ከዓለም የወጡትን በመጋደላቸውም ክፉውን ዐሳብ ድል የነሡትን ምሰሏቸው፡፡

 

ፍለጋቸውንም ካልተከተላችሁ፤ ልጆቻቸው አትባሉምና፤ በመከራቸው ካልመሰላችኋቸው በደስታቸው አትመስሏቸውም፤ በድካማቸውም ካልተባበራችሁ ወደ ቤታቸው አትገቡም.. እነሱን መስላችሁ ኀጢአተኛ አባታችሁን እኔን ደግሞ ምሰሉ፤ ስለትኅርምቱም በመብል በመጠጥ ልባችሁ እንዳይከብድ፣ ሥጋ ከመብላትና ጠጅ ከመጠጣት ተጠበቁ፡፡ ለመመካትም በዓለማዊ ልብስ አታጊጡ፡፡ የመላእክት አስኬማ ከዓለማዊ ሥራ ጋር አይስማማምና፤ ዓለምንም በዓለም ላይ ያለውን ሁሉ አትውደዱ፡፡ ዓለሙም ፈቃዱም ሓላፊ ነውና፡፡ የእግዚአብሔርን ፈቃድ የሚያደርግ ግን ለዘለዓለም ይኖራል፡፡

 

ልጆቼ ሆይ! ትሩፋትን ሁሉ በችኮላ ሠርታችሁ በጎይቱን ሃይማኖታችሁን አስከትሏት፡፡ ለነፍሳችሁ እንጂ ለሆዳችሁ አትገዙ፡፡ ሁላችሁ ወንድማማች ሁኑ፡፡ እርስ በርሳችሁም ተፋቀሩ፤ ከመንፈስ ቅዱስ የሚገኝ ፍቅር ኀጢአትን ያጠፋልና፤ የነፍስና የሥጋን ርኲሰት ያነጻልና፡፡ ይህንንም ብትጠብቁ በእውነት ልጆቼ ናችሁ፡፡ የሕይወትንም ፍሬ የምታፈሩ ትሆናላችሁ፡፡ ወደ እግዚአብሔር ፊት በክብር ትደርሳላችሁ፤…

 

ልጆቼ ሆይ! ሰላም ለእናንተ ይሁን፡፡ እንግዲህ ወዲህ ተሰናበትኳችሁ የእግዚአብሔር ፍቅሩ የክብሩም ባለሟልነት፣ የረዳትነቱም ሀብት ዘወትር ከእኔና ከሁላችሁ ጋር ይኑር ለዘላለም በእውነት ይኑር፡፡” /ገድለ ተክለ ሃይማኖት ዘቀዳሚት ምዕ.54/

 

ጌታችን ለደቀ መዛሙርቱ እናንተን የሚቀበል እኔን ይቀበላል፥ እኔንም የሚቀበል የላከኝን ይቀበላል፡፡ ነቢይን በነቢይ ስም የሚቀበል የነቢይን ዋጋ ይወስዳል፥ ጻድቅንም በጻድቅ ስም የሚቀበል የጻድቁን ዋጋ ይወስዳል፡፡ ማንም ከእነዚህ ከተናናሾቹ ለአንዱ ቀዝቃዛ ጽዋ ብቻ በደቀ መዝሙር ስም የሚያጠጣ፥ እውነት እላችኋለሁ፥ ዋጋው አይጠፋበትም፡፡” /ማቴ.10፥40-42/ ብሎ የተናገረውን መለኮታዊ ቃል ኪዳን ኦርቶዶክሳዊ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ተቀብላ፤ መጋቢት 24 ፅንሰታቸውን፣ ታኅሣስ 24 ቀን ልደታቸውን፣ ጥር 24ን ሰባረ ዐፅማቸውን /የዕረፍታቸውን ቀን ይዞ በዚሁ ወር 24 ይከበራል ሰባረ ዐፅማቸው ከላይ እንደተገለጸው በጥር 4 ነው፡፡/ በግንቦት 12 ቀን ፍልሰተ ዐፅማቸውን ነሐሴ 24 ቀን ዕረፍታቸውን በትላቅ ደስታ ታከብራለች፡፡ ጸሎታቸውና በረከታቸው ረድኤታቸውና ምልጃቸው በመላው ሕዝበ ክርስቲያንና በቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች ሁሉ አድሮ ይኑር ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

 

አርኬ፡-

ሰላም እብል እንበለ አርምሞ በጽዋዔ፡፡ ኪያከ አበ ወኪያከ ረዳኤ፡፡ ተክለ ሃይማኖት መዋዒ እንዘ ትጸንሕ ተስፋ ትንሣኤ፡፡ አጽናዕከ ለቀዊም አእጋረ ክልኤ፡፡ ወእምስቴ ማይ አሕረምከ ጒርዔ፡፡


አሸናፊ የሆንህ ተክለ ሃይማኖት! አባት አንተን ረዳት፥ አንተን ያለዝምታ በጥሪ ሰላም እላለሁ፡፡ የትንሣኤ ተስፋን ስትጠብቅ፤ ሁለት እግሮችን ለቊመት አጸናህ፤ ጒሮሮህንም ውኃ ከመጠጣት አረምኽ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፡- መለከት መጽሔት 18ኛ ዓመት ቁጥር 9

“ኅርየተ ፓትርያርክ በቤተ ክርስቲያን ዘግብጽ ኦርቶዶክሳዊት፤ የፓትርያርክ ምርጫ ታሪክና አፈጻጸም በኮፕት ቤተ ክርስቲያን”

ነሐሴ 23 ቀን 2004 ዓ.ም.

ወልደ ማርያም

የዚህ አጭር ጽሑፍ ዋና ዓላማ በትምህርተ ሃይማኖትና ከሞላ ጎደል በሥርዓተ እምነት ከሚመስሉን አኀት አብያተ ክርስቲያናት መካከል አንዷ የሆነችው የኮፕት ቤተ ክርስቲያን በ2000 ዘመን ታሪኳ የሚመሯትን ፓትርያርኮች እየመረጠች የሄደችበትን ቀኖና ታሪክና ሥልት ጠቅለል ባለ መልኩ ማቅረብ ነው፡፡ ከሌሎቹ አኀት አብያተ ክርስቲያናት የኮፕት ቤተ ክርስቲያንን የምርጫ ቀኖናና ሂደት ዳስሰን ለማቅረብ የፈለግንበት ምክንያት የቤተ ክርስቲያኗ መንበረ ፕትርክና ለ1600 ዘመናት የቤተ ክርስያናችንም መንበረ ፕትርክና ሆኖ የቆየ ከመሆኑ አንጻር በጽሑፉ የሚወሳው ታሪክ የሚቀርበን በመሆኑ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያኗ መንበረ ፕትርክናዋ በመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን ወንጌላዊው ማርቆስ ከተመሠረተበት ጊዜ ጀምሮ እስከ አሁን ድረስ በድምሩ 117 ፓትርያርኮችን እየመረጠች አስቀምጣለች፡፡ ፓትርያርኮቹም የተቀበሉትን ሰማያዊ ሓላፊነት በመያዝ ቤተ ክርስቲያኗ ክፉውንና ደጉን ዘመን አልፋ ዛሬ ካለችበት ደረጃ እንድትደርስ አድርገዋታል፡፡ አሁን ባለችበት ሁኔታ ቤተ ክርስቲያኗ በግብጽና በመላው ዓለም ከ15 እስከ 18 ሚልዮን የሚደርሱ ምእመናን ያሏት ሲሆን እነዚህንም ምእመናን በእረኝነት የሚጠብቁ ከ150 በላይ ሊቃነ ጳጳሳት አሏት፡፡ እነዚህ ሊቃነ ጳጳሳት በመንበረ ፕትርክናው ማእከላዊ አስተዳደር በሚመሩ 54 ያኽል አኅጉረ ስብከት በሊቃነ ጳጳስነት ተመድበው ያገለግላሉ፡፡ ከእነዚህ አኅጉረ ስብከት 15 የሚሆኑት ከግብጽ ውጪ በተለያዩ ክፍላተ ዓለም ተቋቁመው በማገልገል ላይ የሚገኙ ናቸው፡፡

 

ቤተ ክርስቲያኗ በአሁኑ ወቅት ከ41 ዓመታት የፕትርክና አገልግሎት በኋላ መጋቢት 17 ቀን 2012 ዓ.ም. /በዚህ ጽሑፍ የተሰጡት የቀናትና የዓመታት ቁጥር በሙሉ እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር ነው/ ከዚህ ዓለም የተለዩትን 117ኛውን ፓትርያርክ ብፁዕ አቡነ ሲኖዳ 3ኛን ለመተካት በከፍተኛ ዝግጅት ላይ ትገኛለች፡፡ በመሆኑም ቤተ ክርስቲያኗ እ.ኤ.አ. ከ1975 ዓ.ም. ጀምሮ ባላት ቀዋሚ የፓትርያርክ ምርጫ ደንብ መሠረት ሦስት ዕጩዎች ተለይተው አንዱ በዕጣ የሚመረጥበት የመጨረሻ ሥነ ሥርዓት ለመስከረም ቀጠሮ ተይዟል፡፡ ለመሆኑ ይህ ቀዋሚ የፓትርያርክ ምርጫ ደንብ ተረቆ በመጽደቅ ሥራ ላይ ከመዋሉ በፊት ያገለገሉት ፓትርያርኮች እንዴት ተመረጡ? የአመራረጣቸው ሂደትና ቀኖናስ ምን ይመስል ነበር? እያንዳንዱ ሂደትና ቀኖና ተመሳሳይ ነበር ወይስ ልዩነት ነበረው? ይህ ጽሑፍ ለእነዚህ ጥያቄዎች መልስ ይሰጣል፡፡

 

በቤተ ክርስቲያኗ ታሪክ የፓትርያርኮች ምርጫ ምንም እንኳን በመሠረታዊ የተመራጮቹ መመዘኛዎች በአብዛኛው ልዩነት ባይኖርም፤ የምርጫ አፈጻጸም ቀኖናዎች ላይ የሚስተዋሉ ልዩነቶች ነበሩ፡፡ በጉዳዩ ላይ የተጻፉ ጥናቶችንና የፓትርያርኮቹን የሕይወት ታሪክ በማጥናት በቤተ ክርስቲያኗ የ2000 ዘመናት ታሪክ ዘጠኝ ዓይነት የምርጫ ቀኖናዊ ሥልቆች ነበሩ ማለት ይቻላል፡፡ እነዚህን ሥልቶች ከነ አፈጻጸማቸውና ከተመረጡባቸው ፓትርያርኮች ዝርዝር ጋር እንደ ሚከተለው እንመለከታለን፡፡

 

1.    የካህናት ብቻ ምርጫ /Election by Presbyterians of Alexandria/

ይህ ቀኖና ፓትርያርክ የመምረጡን ሓላፊነትና መብት ለካህናት ብቻ የሰጠ ቀኖና ነው፡፡ በተለይ በቤተ ክርስቲያኗ የመጀመሪያዎቹ ዘመናት ያገለገለው ይህ የምርጫ ቀኖና መሠረት ያደረገው በወቅቱ ቤተ ክርስቲያኗ የነበራትን አስተዳደራዊ መዋቅር ነበር፡፡ በተለያዩ መዛግብት ተገልጾ እንደሚገኘው በመጀመሪያዎቹ የአገልግሎት ዘመናቷ ቤተ ክርስቲያኗ ስትመራ የነበረው አባላቱ 12 በሆነ የካህናት ጉባኤ /Presbyterian Council/ አማካይነት ነበር፡፡ በ12ቱ ሐዋርያት ምሳሌነት በቅድስናቸውና በአገልግሎት ልምዳቸው ከማኅበረ ካህናቱ ተመርጠው የሚሾሙት እነዚህ 12 ካህናት ከመካከላቸው የበለጠ የተሻለ ነው ያሉትን አንድ አባት መርጠው በአስራ አንዱ አንበሮተ እድ ሊቀ ጳጳስ አድርገው ይሾሙታል፡፡ ይህ ሊቀ ጳጳስ ጉባኤውን በበላይነት ይመራል፤ ካህናትን ይሾማል፤ አንድ ፓትርያርክ ያለውን ሓላፊነት ሁሉ ይፈጽማል፡፡ በዚህ ዓይነቱ ምርጫ እስከ 12ኛው ፓትርያርክ ዲሜጥሮስ ቀዳማዊ /189-231 ዓ.ም./ ድረስ ቤተ ክርስቲያኗ አንድ ጳጳስ ብቻ ነበራት፡፡

 

በዚህ የምርጫ ሥልት የተመረጠው ሊቀ ጳጳስ በእርግናም ይሁን በጤና መታወክ የተነሣ ኅልፈተ ሕይወቱ በደረሰ ጊዜ ከአስራ አንዱ ውስጥ ብቃት አለው ያለውን መርጦ ያለፈበት አካሄድ ነበር፡፡ ምርጫውንም የሚያውጀው ካህናትና ምእመናን በተሰበሰቡት ጉባኤ ነበር፡፡ ነገር ግን ምንም እንኳን ይሁን ብሎ መርጦት ቢሄድ ተመራጩ በመንብረ ፕትርክናው የሚቀመጠው በካህናት ጉባኤው ታምኖበት ሲጸድቅና በአንብሮተ እዳቸው ሲሾም ብቻ ነበር፡፡ በዚህ ዓይነት ስድስተኛው ፓትርያርክ በቴኦናስ /282-300 ዓ.ም./ እና ሰባተኛው የግብጽ ፓትርያርክ ጴጥሮስ ቀዳማዊ /300-311 ዓ.ም./ ተመርጠው አገልግለው አልፈዋል፡፡

 

ይህ ፓትርያርኮችን የመምረጡ ሥልጣንና ሓላፊነት ካህናት ብቻ የሆነበት ቀኖና እስከ 19ኛው ፓትርያርክ አባ እስክንድር /312-326 ዓ.ም./ ድረስ ሲያገለግል ቆይቶ መንበረ ፓትርያርኩ ከአሌክሳንድርያ ተነሥቶ ወደ ካይሮ ከመዛወሩ ጋር ተያይዞ ተግባራዊነቱ እየቀነሰ መጥቶ በሌላ ቀኖና ተተክቷል፡፡

 

2.    የምእመናን ብቻ ምርጫ / Election by Laity Acting Alone/

ይህ የምርጫ ሥልት በተለይ ቤተ ክርስቲያኗ በእስልምና ወረራ የተነሣ ካህናቷን አጥታ በነበረችበት ዘመን ይፈጸም የነበረ ሲሆን፤ የፓትርያርክ ምርጫ መብት የምእመናን ብቻ የነበረበት ሥልት ነው፡፡ በመሆኑም በዚህ ሥልት ከተመረጡት አምስት ፓትርያርኮች ምእመናንና ዲያቆናት የነበሩ ይገኙባቸዋል፡፡

 

3.    የኤጲስ ቆጶሳት ብቻ ምርጫ /Election by Bishops Acting Alone/

በአፈጻጸሙ ከሮም ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ጋር ተመሳሳይነት ያለው ይህ ሥልት በፓትርያርኮች ምርጫ ምእመናንና ካህናት ቦታ ሳይኖራቸው በኤጲስ ቆጶሳት ብቻ የሚከናወን ነበር፡፡

 

በዚህ ሥልት በድምሩ አራት ፓትርያርኮች ብቻ የተመረጡ ሲሆን እነሱም 19ኛው ፓትሪያርክ አባ እስክድር /312-326 ዓ.ም./፣ 35ኛው ፓትርያርክ አባ ዳምያን /569-605 ዓ.ም./፣ 52ኛው ፓትርያርክ አባ ዮሳብ /830-849 ዓ.ም./ እና 112ኛው ፓትርያርክ አባ ቄርሎስ 5ኛ /1874-1927 ዓ.ም./ ናቸው፡፡

 

4.    በጠቅላላ ስምምነት /Election by General Consensus/

ይህ የምርጫ ቀኖና አፈጻጸሙ ከሊቃነ ጳጳሳት፣ ከካህናት ተወካዮችና ከሌሎች መሪዎች የተውጣጡ መራጮች ካሉት ሊቃነ ጳጳሳት አንዱን በሙሉ ስምምነት መርጠው የሚሾሙበት ቀኖና ነበር፡፡ በዚህ ቀኖና ሠላሳ አምስት ፓትርያርኮች ተመርጠው አገልግለው አልፈዋል፡፡ የፓትሪያርኮችን ዝርዝር ከጽሑፉ መጨረሻ ከሚቀርበው ሠንጠረዥ ይመለከቷል፡፡

 

5.    በሓላፊው ፓትርያርክ ምርጫ /Election through the Appointment of the Predecessor/

በዚህ የምርጫ ቀኖና በዕድሜ መግፋትም ይሁን በጤና መታወክ የተነሣ ኅልፈተ ሕይወቱን በሚጠባበቅበት አልጋ ላይ /Death bed/ ሆኖ የሚጠብቀው ፓትርያርክ ካሉት ጻጳሳት ወይም መነኮሳት ውስጥ የበለጠ ይመጥናል ያለውን መርጦ የሚያስቀምጥበት ቀኖና ነው፡፡ ይህንን ቀኖናዊ የምርጫ ሥልት ቤተ ክርስቲያኗን ያጠኑ ሊቃውንት የፓትሪያርክ የመጨረሻ ምኞት /patriarchal Death bed wish/ ይሉታል፡፡ እንደ ቤተ ክርስቲያኗ ሊቃውንት ትረካ የዚህ ቀኖና መሠረቱ የመጀመሪያው የቤተ ክርስቲያኗ መሥራችና ፓትርያርክ ቅዱስ ማርቆስ በእሱ መንበር ተቀምጦ ቤተ ክርስቲያኗን ይመራ ዘንድ ሁለተኛውን ፓትርያርክ አባ አንያኖስን /68-85 ዓ.ም./ መርጦ ያለፈበት ታሪክ ነው፡፡ በዚህ ቀኖናዊ የምርጫ ሥልት በድምሩ ሰባት ፓትርያርኮች ተመርጠዋል፡፡ ይህ ሥልት በብቃት ሳይሆን ለፓትርያርኩ ካላቸው ቅርበት የተነሣ እንዲመረጡ ያደረጋቸው አንዳንድ አባቶች እንዳሉ በቤተ ክርስቲያኗ ታሪክ ይወሳል፡፡ በዚህ ረገድ በምሳሌነት የሚጠቀሰው ሠላሳ ስምንተኛው ፓትርያርክ አባ ቢንያም ቀዳማዊ /622-661 ዓ.ም./ ነው፡፡ ይህ ፓትርያርክ ሲመረጥ በቅድስናም ይሁን በአገልግሎት ልምድ ከእነሱ የተሻሉ የነበሩ ቢሆንም በዘመነ ፕትርክናው ያገለግለው የነበረው ሓላፊ ፓትርያርክ ስለመረጠው እንደተሾመ ተጽፏል፡፡

 

6.    መለኮታዊ ምርጫ ወይም ራእይ /Election by Divine Appointment or vision/

እንደ ቤተ ክርስቲያኗ ሊቃውንት አስተምህሮ ይህ ሥልት የተወሰደው የመጀመሪያው ፓትሪያርክ ቅዱስ ማርቆስ ወንጌላዊ በመለኮታዊ ጥበብ ከተሾመበት አካሄድ ነው፡፡ ይህ ሥልት በተለይ በሓላፊው ፓትርያርክ ወይም ለእሱ ለሚቀርቡና በፓትርያርክ ምርጫው ተሳትፊ በሆኑ አካላት በሚታይ ራእይ ተመሥርቶ ፓትርያርክ የሚመረጥበት ዘዴ ነበር፡፡ ለምሳሌ በእርግና አልጋው ላይ የነበረው 11ኛው ፓትርያርክ አባ ዩልየስ /189-231 ዓ.ም./ መልአኩ ተገልጦ “ነገ ወደ መንበረ ፕትርክናው መጥቶ ዕቅፍ ወይን የሚያበረክትልህ እሱ በመንበርህ ይተካል” እንዳለውና በወቅቱ በግብርና የገዳም ማኅበሩን ሲያገለግል የነበረው ዲሜጥሮስ ባልተለመደ ሁኔታ ማሳው ላይ የወይን ተክል በማግኘቱ “ይህስ ለቅዱስ ፓትርያርክ ይገባል” ብሎ ቆርጦ በዕቅፉ ወስዶ ስላበረከተለት መንበረ ፓትርያርኩን ተረክቦ ቤተ ክርስቲያኗን ለ42 ዓመታት /189-231 ዓ.ም./ እንዳገለገለ መጻሕፍት ያስረዳሉ፡፡ በተመሳሳይም 46ኛውን ፓትርያርክ ለመምረጥ ኤጲስ ቆጶሳት ካህናትና ምእመናን ተሰብስበው ሦስት ዕጩዎችን ቢያቀርቡም በመራጮቹ መካከል ከፍተኛ ልዩነትና ጭቅጭቅ በተነሣ ጊዜ ከመካከላቸው አንዱ የሆነው ሊቀ ዲያቆን፤ አባ ኽኢል የተባለው ሰው ለመንበሩ ብቃት እንዳለው ራእይ በማየቱ በእሱ ሕልም ተመርተው በሙሉ ስምምነት እንደሾሙት ተጽፏል፡፡

 

7.    ዕጣ የማውጣት ምርጫ /Election through Casting of Lots/

ይህ ቀኖና አስራ አንዱ ሐዋርያት በይሁዳ ምትክ ከእነሱ ጋር ይደመር ዘንድ ማትያስን የመረጡበትን አካሄድ በሞዴልነት በመጠቀም በቤተ ክርስቲያኗ የታሪክ ዘመናት እንደታየው ይህ ዘዴ ተግባር ላይ ሲውል የነበረው በዕጩዎች መካከል እኩል ተቀባይነትና ቅድስና ኖሮ አንዱን ከሌላው ለመለየት አስቸጋሪ ሲሆን ወይም ዕጩዎች ያገኙት ድምጽ አንድ ዓይነት ሲሆንና /ምሳሌ ሰባ አንደኛው ፓትርያርክ አባ ሚካኤል /1145-1146 ዓ.ም/ እና በዕጩዎቹ ደጋፊዎች መካከል ከፍተኛ ሽኩቻና ጸብ ሲኖር /ምሳሌ 48ኛው ፓትርያርክ ዮሐንስ አራተኛ /775-799 ዓ.ም./ ነው፡፡ የዕጣ አወጣጥ ሥርዓቱም በሰንበት ቀን የዕጩዎቹ ስም በታሸገ ኢንቨሎፕ ከመንበሩ ላይ ይቀመጥና ጸሎተ ቅዳሴ እንዲሁም ቀኖና የሚያዝዘው ጸሎት ሁሉ ተደርጎ ሲያበቃ አንድ ሕጻን ከአስቀዳሾች መካከል ቀርቦ ዓይኑን በጨርቅ ከታሰረ በኋላ አንዱን ያወጣል፡፡ ስሙ የወጣውም ቀጣዩ የቤተ ክርስቲያኗ ፓትርያርክ ሆኖ ይሾማል፡፡ በዚህ ቀኖናዊ ሥልት በአጠቃላይ አሥር ያህል ፓትርያርኮች ተመርጠው አገልግለው አልፈዋል፡፡

 

ከዚህ በታች የምናያቸው ሁለት የምርጫ ሂደቶች በቤተ ክርስቲያኗ ታሪክ በቀኖናዊ ሥልትነት የተመዘገቡ ሳይሆኑ፤ ፓትርያርኮች ተመርጠው ያለፉባቸው አካሄዶች ናቸው፡፡

 

8.    የመንግሥት ጣልቃ ገብነት /Strong Intervention by Government/

የኮፕት ቤተ ክርስቲያን ዛሬ ድረስ ዘልቀው ከሚያስቸግሯት ፈተናዎች አንዱ በሀገሪቱ መንግሥት ያለባት ጫና ነው፡፡ ይህ የገዥዎች ቀንበር በቤተ ክርስቲያኗ ጫንቃ ላይ የወደቀው ሀገሪቱ በአረብ እስላሞች እጅ ከወደቀችበት 640 ዓ.ም. ጀምሮ ነው፡፡ ሀገሪቱን የሚመራው ኢስላማዊ መንግሥት በቤተ ክርስቲያኗ ላይ ከሚያሳድረው ተጽዕኖ መገለጫዎች አንዱ በቤተ ክርስቲያኗ የፓትርያርክ ምርጫ ላይ የሚያሳድረው ተጽዕኖና የወሳኝነት ሚና ነበር፡፡ እሱም ቢሆን ከመንግሥቱ ጣልቃ ገብነት ሳይወጣ፤ ቤተ ክርስቲያኗ በራሷ አካሄድ ይሆነኛል ያለችውን ብትመርጥም ተመራጩ አባት ፓትርያርክ ሆኖ የሚሠየመው ስሙ ወደ ሀገሩ ገዥ ተልኮ ሲጸድቅ ብቻ ነበር፡፡ በዚህ ዓይነት በቤተ ክርስቲያኗ ታሪክ ስድስት ያህል ፓትርያርኮች ተመርጠው አገልግለው አልፈዋል፡፡ በእርግጥ ቤተ ክርስቲያኗ በፓትርያርክ ምርጫ ከፍተኛ የመንግሥት ተጽዕኖ ነበረባት ቢባልም፤ በወቅቱ የነበሩት አባቶችና ምእመናን ተጽዕኖውን በመቋቋም የቤተ ክርስቲያናቸውን ክብር ለማስጠበቅ ሞክረዋል፡፡ በዚህ ረገድ ከሊቃነ ጳጳሳቱ፣ ማኅበረ ካህናቱና ምእመናኑ ፈቃድና ይሁንታ ውጭ በወቅቱ ለነበሩት ገዥዎች በነበረው ቀረቤታና አገልግሎት በመንግሥት ቀጥተኛ ምርጫና ትእዛዝ እንዲመረጥ የቀረበውን ሰባ አምስተኛውን ፓትርያርክ አባ ቄርሎስ 3ኛ /1235-1243 ዓ.ም./ እንዳይመረጥ ከፍተኛ ተጋድሎ አድርገዋል፡፡ በዚህ የተነሣም ምንም እንኳን የኋላ ኋላ መንግሥት አሸንፎ አባ ቄርሎስ ፓትርያርክ ሆኖ ቢመረጥም፤ ለ19 ዓመታት መንበሩ ባዶ ሆኖ ታግለዋል፡፡

 

9.    በአጋጣሚ /Election by Coincidence or Chance/

ይህ የምርጫ ሂደት መራጮቹም ይሁኑ ተመራጩ ባላሰበበት ሁኔታ በአጋጣሚ ያልታሰቡ መነኮሳት ተመርጠው ለከፍተኛው ሥልጣን የበቁበት ሂደት ነው፡፡ ለዚህ ሂደት በምሳሌነት በተደጋጋሚ ተጠቅሶ የሚገኘው የ64ኛው ፓትርያርክ አመራረጥ ሂደት ነው፡፡ 63ኛው ፓትሪያርክ ከዚህ ዓለም በሞት እንደተለየ ሲሰማ፤ አንድ ባዕለ ጸጋ በዘመኑ ለነበረው ኸሊፋ /የግብጽ ገዥ/ ብዙ ገንዘብ ከሰጠው በኋላ ባለፈው ፓትርያርክ መንበር እንዲሾመው ይጠይቀዋል፡፡ ኸሊፋውም የባዕለ ጸጋውን ገንዘብና ጥያቄ ተቀብሎ በካይሮ ያሉት አባቶች ትእዛዙን ይፈጽሙ ዘንድ ደብዳቤ አስይዞ ይልከዋል፡፡ በዚህ ተጨንቀው የተቀመጡ አባቶችም ነጋዴውን በመጠባበቅ ላይ ሳሉ አንድ በቅድስናውና በአገልግሎት ትጋቱ የታወቀ መነኩሴ የሸክላ ድስት ይዞ አባቶች ተሰባስበው ወደ ተቀመጡበት አዳራሽ ይገባና እየጮኸ ድስቱን ከደረጃ ላይ በኀይል ይጥለዋል፡፡ ደጋግሞም እያነሳ ይጥለዋል፡፡ ነገር ግን ባልተለመደ ሁኔታ ድስቱ ሳይሰበር ቀረ፡፡ ይህንን ያዩና በጭንቀት ውስጥ የነበሩ አባቶች ባዕለ ጸጋው ከመድረሱ በፊት ቶሎ ብለው አባ ዘካርያስ /1004-1032/ ብለው መነኩሴውን እንደ ሾሙት በቤተ ክርስቲያኗ የታሪክ መዛግብት ሰፍሮ ይገኛል፡፡

 

ከላይ ባየናቸው ቀኖናዊ የምርጫ ማስፈጸሚያ ሥልቶችና ሂደቶች በእያንዳንዱ የተመረጡትን አባቶች ዝርዝር በሚከተለው ሠንጠረዥ ማየት ይቻላል፡፡

 

ተ.ቁ

ቀኖናዊ የምርጫ ሥልት

ወይም ሂደት

በሥልቱ ወይም በሂደቱ የተመረጡ አባቶች ብዛት

የተመረጡት ፓትሪያርኮች

ተራ ቁጥር

1

የካህናት ብቻ ምርጫ

16

4፣5፣6፣7፣8፣9፣10፣11፣12፣13፣14፣

15፣16፣17፣18፣

2

የምእመናን ብቻ ምርጫ

5

44፣70፣74፣77፣101

3

የኤጲስ ቆጶሳት ብቻ ምርጫ

4

19፣35፣52፣112

4

በጠቅላላ ስምምነት

35

20፣22፣24፣28፣36፣37፣43፣45፣

47፣51፣53፣54፣55፣61፣62፣67፣

68፣69፣72፣73፣76፣80፣81፣83፣

87፣95፣100፣106፣107፣109፣

110፣111፣113፣114፣115

5

በሓላፊው ፓትርያርክ ምርጫ

7

2፣21፣38፣39፣49፣50፣88

6

መለኮታዊ ምርጫ ወይም ራእይ

4

1፣12፣46፣82

7

ዕጣ የማውጣት ምርጫ

10

3፣48፣71፣102፣103፣104፣

105፣108፣116፣117

8

የመንግሥት ጣልቃ ገብነት

6

27፣31፣33፣41፣75፣78

9

በአጋጣሚ

3

42፣63፣64

 

በየትኛው ሥልት ወይም ሂደት እንደተመረጡ የማይታወቁ

27

 

 

ድምር

117

 

 

የፓትርያርክ ምርጫ ሥርዓትና አፈጻጸም በግብጽ ቤተ ክርስቲያን ዛሬ

ከላይ ባየናቸው ሥልቶች ፓትርያርኮቿን እየመረጠች 2000 ዓመታት የተጓዘችዋ ቤተ ክርስቲያን ዛሬ በቅርቡ ያለፉት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሲኖዳ 3ኛና እሳቸው የተኳቸው አባ ቄርሎስ ምርጫ ወቅት ሥራ ላይ ውሎ የተፈተነ ቀዋሚ የፓትርያርክ ምርጫ ደንብ አላት፡፡ የዚህን ደንብ ትርጉም ተግባር ላይ ከመዋሉ በፊትና ከዋለ በኋላ ያጋጠሙትንና እያጋጠሙት ካሉት ተግዳሮቶች ጋር በሚቀጥለው አቀርባለሁ፡፡

 

ምንጭ:-

Atiya, Aziz S.ed., The Coptic Encyclopedia.8 vols. New York:macmillan,1991.

E l- Masri, Iris Habib. The Story of the Copts: The true Story of Christian in Egypt. Cairo: Coptic Bishopric of African Affairs.1987.

Evetts. B. ed “History of the patriarchs of the Coptic Church of Alexandria” Patrologia Orientalis I.4, Paris,1984

Meinardus, O.F.A. Christian Egypt: Faith and Life. Cairo: American University in Cairo Press, 1970.

Saad Michael Saad and Nardine Miranda Saad. “Electing Coptic Patriarchs: A Diversity of Tradition”

Bulletin of St. Shenouda the Archimanrite Coptic Society 6,1999-2000, pp.20-32.

“ዘይሁብ መርሐ ርቱዐ ለቤተ ክርስቲያን – ለቤተ ክርስቲያን ቅን መሪ የሚሰጥ”

ቤተ ክርስቲያን የምንላት ወልድ ዋሕድ ኢየሱስ ክርስቶስ ከፍጹምና ከማይነገር ፍቅሩ የተነሣ ሰው እስከ መሆን፣ ሰው ሆኖም በዚህ ዓለም ከኃጢአት በስተቀር እንደ ሰው መኖርን፣ ከዚያም በቀራንዮ ቅዱስ ሥጋውን እስኪቆርስላትና ክቡር ደሙን እስኪያፈስላት ድረስ የደረሰላትና የመሠረታት የምእመናን አንድነት (ጉባኤ) ናት፡፡ “ወነአምን በአሐቲ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንተ ላእለ ኩሉ ጉባኤ ዘሐዋርያት” የምንለው ለዚህ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን በወንጌል መሠረትነት በኢየሱስ ክርስቶስ ራስነት በምእመናን አካልነት የተመሠረተች ጉባኤ ናት፡፡
ቤተ ክርስቲያን ስንል የዚህ ዓለም ተጋድሏቸውን በድል አጠናቅቀው ወደ እግዚአብሔር የሄዱ ቅዱሳን (ሐዋርያት፣ ሰማዕታት፣ ሊቃውንት፣ …) እና ገና በዚህ ዓለም በተጋድሎ ላይ ያሉት የምእመናን አንድነት (ጉባኤ) ናት፡፡ በሰማይ ያለችው ቤተ ክርስቲያን (ጉባኤ) የዚህ ዓለም ጣጣቸውን ጨርሰው የሄዱ፣ ድል አድርገው የድል አክሊላቸውን ለመቀበል እርሱ የወሰነውን ጊዜ የሚጠባበቁ ቅዱሳን ኅብረት ስለሆነች አትናወጽም፤ ስለሆነም ሊቃውንት ይህችን ቤተ ክርስቲያን ድል አድራጊዋ ቤተ ክርስቲያን (Church Triumphant) ይሏታል፡፡ ገና በዚህ ዓለም በጉዞና በፈተና ላይ ያለችውን የአንዲቷ ቤተ ክርስቲያን አካል የሆነችውን ጉባኤ (ቤተ ክርስቲያን) ደግሞ ገና በተጋድሎ ላይ ያለች ቤተ ክርስቲያን (Church Militant) ይሏታል፡፡
በዚህ ዓለም ያለችው ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያት በባሕር ላይ በታንኳ እየሄዱ ሳለ ጌታችን አብሯቸው በመካከላቸውና በታንኳው ውስጥ እያለ፣ ነገር ግን በኃይለኛ ማዕበል ትናወጥ እንደ ነበረችው ታንኳ በተለያዩ ፈተናዎች ትናወጻለች፡፡ አንዳንድ ጊዜም በውስጧ ያለው ጌታ የማይሰማና የተዋት፣ መከራዋን እያየ ዝም ያላት፣ ባለቤት የሌላት እስክትመስል ድረስ በውስጧ ያሉና በተለያዩ ነገሮች ተጨንቀው የሚያማርሩና የሚያዝኑ ልጆቿም ሰሚ የሌላቸው የሙት ልጆች እስኪመስሉ ድረስ ባለቤቷ ኢየሱስ ክርስቶስ ዝም ይላል፡፡ ሐዋርያትንም “ስንጠፋ አይገድህምን?” እስኪሉ ያደረሳቸው ይህ ነበር፡፡ ማቴ. 8፡23-27
የአንዲቷ ቤተ ክርስቲያን አካል የሆነችው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አምስተኛ ፓትርያርክ የነበሩት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ማረፋቸው ይታወቃል፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን የእርሳቸውን ነፍስ ከቅዱሳን ጋር ይደምርልን እያለች ተተኪውን ስድስተኛውን ፓትርያርክ የመምረጥ ከባድ ሥራ ደግሞ ከፊቷ ተደቅኗል፡፡ ይህ ሥራ ሂደቱና ውጤቱ ቢያንስ ቢያንስ ለሚመጡት የተወሰኑ ዓመታት በቤተ ክርስቲያናችን አካሄድ ላይ የራሱ የሆነ ተጽእኖ የሚኖረው መሆኑ የታወቀ ነው፡፡ የዚህ ጽሑፍ ዓላማም በዚህ ታላቅ ወሳኝ ወቅት ላይ እያንዳንዳችን ምን ብናደርግ እንደሚሻል አጠንክረን እንድናስብ ሕሊናችንን ለማነሣሣት ያህል ነው፡፡
ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የባለቤቷ የኢየሱስ ክርስቶስ ሙሽራ ስለሆነች ጠባቂዋና ተንከባካቢዋ እርሱ ራሱ ነው፡፡ ምንም እንኳ እርሱ በሚያውቀውና በተለያዩ ምክንያቶች እንድትፈተን ቢፈቅድም እንድትጠፋ ግን አይተዋትም፡፡ ይህ ማለት ግን በውስጧ ያሉ አባላት በጥርጥርና በልዩ ልዩ ፈተናዎች አይሰናከሉም ማለት ግን አይደለም፡፡ ምንም ቢሆን ግን ቤተ ክርስቲያን የራሱ የክርስቶስ አካሉ እንደ መሆኗ ራሷ የሆነ እርሱ ለአካሉ ለምእመናን የሚያስፈልገውን ያውቃል፣ ያዘጋጃል፣ ይሰጣል፡፡ ለዚህ ነው በጸሎተ ኪዳናችን ላይ “ዘይሁብ መርሐ ርቱዐ ለቤተ ክርስቲያን – ለቤተ ክርስቲያን ቅን መሪ የሚሰጥ” የተባለው፡፡
ነገር ግን ችግር የሚሆነው ቤተ ክርስቲያን የማን መሆኗን ዘንግተን ባለቤቷና ራሷ የሆነው መድኃኒታችን ኢየሱስ  ክርስቶስ እርሱ ራሱ የሚሆናትን ቅን መሪ እንዲሰጣት ከመጠየቅና ከመማጸን አልፈን እኛው ራሳችን መሪ እንስጥሽ ወደሚል ዝንባሌና አስተሳሰብ ስንሄድ ነው፡፡ እያንዳንዱ ሰው እንደየ እውቀቱና አመለካከቱ ለክርስቶስ ሙሽራ ለሆነችው ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን “እንዲህ ቢሆን፣ እገሌ ቢሆን፣ . . . ” ወደሚል ነገር መምጣት በሽታውን ሳይረዳ እንዲሁ በይመስላል መድኃኒት እንደሚያዝ ሰው መሆን ነው፡፡ በሽታውን ሳይመረምሩና ለመረዳት ጥረት ሳያደርጉ እንዲሁ በግምት፣ በአውቀዋለሁ ባይነትና በግዴለሽነት የሚታዘዘውን እንዲህ ያለውን መድኃኒት መውሰድ ምናልባትም ካለመውሰድ በባሰ ጤናን ሊያውክና ሕማምንም ሊያባብስ ይችላልና፡፡
ታዲያ መሥራቿና ባለቤቷ ኢየሱስ ክርስቶስ አካሉ ለሆነችው ለቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ቅን መሪ እንዲሰጣት የእኛ ድርሻ ምን ቢሆን ይሻል ይሆን? ምንስ እናድርግ?
1. መሪ የመስጠቱን ሥራ ለራሱ ለእግዚአብሔር እንስጠው – እኛ ሳንሆን ራሱ ይምረጥልን
እስራኤላውያን ከግብፅ ከወጡ በኋላ መሪያቸውና ንጉሣቸው እግዚአብሔር ሆኖ በተለያዩ መሳፍንት አማካይነት ያስተዳድራቸው ነበር፡፡ መሳፍንቱም የባለ ሥልጣን ወግ ማዕረግ የሌላቸው ከሕዝቡ እንደ አንዱ ሆነው የሚስተዳድሩ፣ ጦርነት ሲሆንና አስፈላጊ በሚሆኑ ዋና ዋና ጉዳዮች ላይ ብቻ የሚመሩ ነበሩ፡፡ ከሙሴ አንስቶ እሰከ ሳሙኤል ዘመን ድረስ ለ450 ዓመታት በዚህ ዓይነት ሁኔታ እየተመሩ ኖሩ፡፡ ሳሙኤልም ምስፍናና ክህነቱን ደርቦ ሕዝቡን አንደ ካህንነቱ ከእግዚአብሔር ጋር እያገናኘ፣ እንደ መሳፍንነቱ ደግሞ አስተዳደራዊ የሆኑ ጉዳዮቹን ያሰዳድራቸው ነበር፡፡ የሐዋ.13፡20-21
እነርሱ በዚህ ሁኔታ እየኖሩ ሳለ በአካባቢያቸው የሚኖሩ የተለያዩ አሕዛብ ደግሞ የራሱ የሆነ የንግሥና ሥርዓት፣ አፋሽ አጎንባሽ፣ ሠረገላና ሠራዊት፣ ሽቶ ቀማሚዎች፣ ወጥ ቤቶችና እንጀራ አበዛዎች ያሏቸው፣ ሕዝቡን የሚያስገብሩ ነገሥታት ነበሯቸው፡፡ እስራኤላውያን በአሕዛብ በመቅናት ንጉሣቸው እግዚአብሔር መሆኑ ቀርቶ እንደ ሌሎቹ ጎረቤቶቻቸው ከመካከላቸው አንዱን እነዲያነግሥላቸው በሳሙኤል በኩል ጠየቁ፡፡ በዚህ ጊዜ ሳሙኤል ወደ እግዚአብሔር ጸለየ፡፡ እግዚአብሔርም ሳሙኤልን አለው፡-
“በእነርሱ ላይ እንዳልነግሥ እኔን እንጂ አንተን አልናቁምና በሚሉህ ነገር ሁሉ የሕዝቡን ቃል ስማ፡፡ ከግብጽ ካወጣኋቸው ቀን ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ እኔን ትተው እንግዶች አማልክት በማምለካቸው እንደ ሠሩት ሥራ ሁሉ እንዲሁ በአንተ ደግሞ ያደርጉብሃል፡፡ . . . ለሕዝቡም በእናንተ ላይ የሚነግሠው የንጉሡ ወግ ይህ ነው ብለህ ንገራቸው፡- ወንዶች ልጆቻችሁን ወስዶ ሰረገለኞችና ፈረሰኞች ያደርጋቸዋል፣ . . . ሎሌዎቻችሁንና ገረዶቻችሁን ከከብቶቻችሁና ከአህዮቻችሁም መካከል መልካሞቹን ወስዶ ያሠራቸዋል፡፡ ከበጎቻችሁና ከፍየሎቻችሁ አሥራት ይወስዳል፤ እናንተም ባሪያዎች ትሆኑታላችሁ፡፡ በዚያም ቀን ለእናንተ ከመረጣችሁት ከንጉሣችሁ የተነሣ ትጮኻላችሁ፤ በዚያም ቀን እግዚአብሔር አይሰማችሁም፡፡” 1 ሳሙ. 8፡10-18
እንደ ልመናቸው ንጉሥ ሰጣቸው፣ ሳኦልን አነገሠላቸው፡፡ ሆኖም እግዚአብሔር አስቀድሞ እንደ ነገራቸው ብዙም ሳይቆይ ንጉሦቻቸው ለሕዝበ እስራኤል ዋናው የጥፋታቸው መሪዎች በመሆን የጥፋታቸውን ጎዳና ደኅና አድርገው ጠርገውላቸዋል፡፡ በንጉሥ ሰሎሞን ኃጢአት ምክንያት በልጁ በሮብአም ዘመን አንድ የነበረው ሕዝብ ከሁለት ተከፈለ፤ አሥሩ ነገድ የእስራኤል መንግሥት ተብሎ በሰሜን፣ ሁለቱ ነገድ ደግሞ በደቡብ የይሁዳ መንግሥት ተብሎ በ928 ቅድመ ልደተ ክርስቶስ ዳግመኛ አንድ ላይሆኑ ተለያዩ፡፡
ቀጥሎም የአሥሩ ነገድ ንጉሥ የነበረው ኢዮርብዓም በግዛታቸው በስሜንና በደቡብ ጫፍ ላይ በዳንና በቤቴል ጣዖት አቁሞ ከዚያ በፊት ይደረግ እንደ ነበረው ሕዝቡ ወደ ኢየሩሳሌም ሄዶ በታቦተ ጽዮን ፊት በቤተ መቅደሱ መሥዋዕት አቅርቦ አምላኩን እግዚአብሔርን አዘክሮ እንዳይመለስ በዚያው በሰሜኑ ግዛት ብቻ ተገድቦ እንዲቀር ለማድረግ ሲል ባቆማቸው ጣዖታት ሕዝቡን እግዚአብሔርን ከማምለክ ጣዖት ወደ ማምለክ እንዲያዘነብል አደረገው፡፡ ከዚሁም ጋር ንጉሣቸው ኢዮርብዓም እንደ ሕጉ መሠረት ካህናትን ከሌዋውያን ሳይሆን ሌዋውያን ካልሆኑት መካከል ለራሱ የሚመቹትን ካህናት ናቸው ብሎ መረጠ፣ በዓል የሚከበርበትን ቀን ለወጠ፣ በአጠቃላይ በኦሪቱ የተሰጠውን ነገር ሁሉ ገለባበጠው፡፡
እስራኤላውያን አስቀድሞ የንጉሥ አንግሥልን ምርጫቸው ምን እንደሚያስከትል በግልጽ እንደ ተነገራቸው ሆነባቸው፡፡ የሰሜኑ ግዛት የአሥሩ ነገድ ነገሥታት ኢዮርብዓም በጀመረው ከእግዚአብሔር የመለየትና ጣዖት የማምለክ የጥፋት ጎዳና እየገፉበት ሄዱ፡፡ ከዚያም በኋላ እነ አክአብና ኤልዛቤል ክህደቱና ኃጢአቱ፣ ግፉና ዓመጹ መሥፈሪያውን ቶሎ እንዲሞላ እያቻኮለው ሄደ፡፡ በዚያ የጥፋት ቁልቁሊት በፍጥነት በመቀጠል የእስራኤል መንግሥት ለሁለት በተከፈለ በ210 ዓመት (በ718 ቅድመ ልደተ ክርስቶስ) በአሶራውያን ተማርከው ተወሰዱ፡፡ 2 ነገ. ምዕ. 17 ከዚያ በኋላ የአሥሩ ነገድ ነገር የውኃ ሽታ ሆኖ ቀረ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ስለ አሥሩ ነገድ መማረክ ይነግረናል እንጂ ከዚያ በኋላ የት እንደ ደረሱና ምን እንደ ሆኑ አይነግረንም፡፡ በመጽሐፈ ዕዝራና ነህምያ ከምርኮ ስለ መመለሳቸው የተጻፈላቸው በኋላ የተማረኩት ሁለቱ ነገድ ናቸው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ከተነገሩና ምሥጢራቸው ካልተፈታ ታሪኮች አንዱ ይህ የአሥሩ ነገድ ጉዳይ ነው፡፡ እንግዲህ ያ የወደዱትና ጓጉተውና ሽተው የለመኑት የንጉሥ አንግሥልን ጥያቄ ነገር ፍጻሜያቸው እንዲህ አሳዛኝ እንዲሆን አድርጎታል፡፡
በዚሁ ንጉሥ የማንገሥ ጉዳይ ነቢዩ ሳሙኤል ከእግዚአብሔር ፊት በተናቀው በሳኦል ፋንታ የሚቀባውን ሊፈልግ ወደ ቤተ ልሔም ሄዶ ወደ እሴይ ቤት ገብቶ በዚያ የነበሩትን የእሴይን ልጆች ተራ በተራ ሲያልፉ ዓይኑ ኤልያብ ላይ አርፎ ነበር፡፡ ኤልያብ በሰው አስተሳሰብ መልከ መልካምና ተክለ ቁመናው የሚስብ ስለነበር ነቢዩ ሳሙኤል እርሱን ሲመለከት “በእውነት እግዚአብሔር የሚቀባው በፊቱ ነው” አለ፡፡ እግዚአብሔር ግን ሳሙኤልን፡- “ፊቱን የቁመቱንም ዘለግታ አትይ፤ ሰው እንዲያይ እግዚአብሔር አያይምና ናቅሁት፤ ሰው ፊትን ያያል፣ እግዚአብሔር ግን ልብን ያያል” አለው፡፡ ሌሎቹም የእሴይ ልጆች እነ አሚናዳብ፣ ሣማን፣ … በፊቱ አለፉ፡፡ ሆኖም እነዚያ ሁሉም “ይህን ደግሞ እዘለግታ አትይ” የሚል ተግሣጽ አከል ነገር የተናገረው ለዚህ ነበር፡፡ እንግዲህ እንዲህ ያሉ ታላላቅ አባቶች እንኳ እግዚአብሔር ያዘጋጀውንና የመረጠውን ለማወቅ ይህን ያህል የሚቸገሩና ለዚህ ጥሪ የማይሆኑ ብዙ ሰዎችን አጣርተው (በፊታቸው አሳልፈው) መተው ያለባቸው ከሆነ ለእኛማ ምን ያህል ከባድ ይሆን?
ይህ ማለት እኛ መሥራት ያለብንን ሥራ መሥራት የለብንም ማለት አይደለም፡፡ ነገር ግን እንዲህ ዓይነት ቤተ ክርስቲያንን በአባትነት የሚመራ፣ ለመንጋው ታማኝ የሆነና መንጋውም የሚወደውና የሚያፈቅረው፣ ምንደኛ ያይደለ እረኛ፣ ጌታ ሳይሆን አገልጋይ፣ ለራሱ ሥልጣንና ክብር ሳይሆን ለእግዚአብሔር ክብር የሚቀና፣ ውስብስብ የሆነውን ዓለም በመስቀል ተደግፎ የሚሻገርና የሚያሻግር�ግዚአብሔር አልመረጠውም” እየተባሉ በፊቱ አለፉ፡፡ እግዚአብሔር የመረጠው አባቱ እንኳ ሳይቀር ለዚህ ይሆናል ብሎ ያላሳበው፣ ከዚህም የተነሣ ከመሥዋዕቱ ጥሪና ከበዓሉ ሥርዓት ለይቶ በጎችን እንዲጠብቅ በዱር የተወው ዳዊት ነበር፡፡
የሰው የምርጫ መለኪያና የእግዚአብሔር የምርጫ መለኪያ ምን ያህል የተራራቁና የተለያዩ እንደ ሆኑ እናስተውል፡፡ ሌላው ቀርቶ ክህነት ከምስፍና ደርቦ የያዘው ታላቁ ነቢይ ሳሙኤል እንኳ ኤልያብን ሲያየው ገጽታውን በመመልከት ብቻ ወዲያዉኑ ደስ ብሎት “በእውነት እግዚአብሔር የሚቀባው በፊቱ ነው” እስኪል ያደረሰው በውጫዊ ነገር በመሳቡና በመመሰጡ ነበር፡፡ እግዚአብሔር በዚህ ጊዜ “ኢትርአይ ግርማ ርእየቱ ለኤልያብ – የኤልያብን ፊቱን የቁመቱንም �� ቤተ ክርስቲያንን የሚመራ፣ ራሱ ግን በእግዚአብሔር የሚመራ ሰው ማግኘት ለሰው ከባድ ስለሆነ ነው ሁሉን ለሚያውቀው ለእርሱ መተው ከሁሉም የተሻለ አማራጭ የሚሆነው፡፡ ራሱ ባለቤቱም ይህን ሲያስተምረን “መኑ እንጋ ገብር ምእምን ወጠቢብ ዘይሠይሞ እግዚኡ ውስተ ኩሉ ቤቱ ከመ የሀቦሙ ሲሳዮሙ በጊዜሁ – ምግባቸውን በየጊዜው ይሰጣቸው ዘንድ ጌታው በቤተ ሰዎቹ ላይ የሚሾመው ልባምና ታማኝ ባሪያ ማን ነው?” ሲል የጠየቀው እንዲህ ያሉ ታማኝ አገልጋዮችን (ጌቶችን አላለም) ማግኘት ምን ያህል ከባድ እንደሆነ ሲያስተምረን ነው፡፡ ማቴ. 24፡45
ቅዱሳን ሐዋርያት በይሁዳ ቦታ የሚተካና ከአሥራ ሁለቱ ሐዋርያት ገብቶ የሚቆጠር ሰው ሊመርጡ ሲሉ ሁለት ሰዎችን አቀረቡና ከሁለቱ አንዱን እግዚአብሔር እንዲመርጥላቸው ዕጣ ጣሉ፡፡ ዕጣውም ለማትያስ ወደቀ፡፡ ታዲያ ሐዋርያት እንዲህ ምርጫውን ለእግዚአብሔር ከሰጡ እኛ ለእርሱ የማንሰጥበት ምክንያት ምን ይሆን? የሐዋ. 1፡21-26
ስለሆነም እኛ እያንዳንዳችን እግዚአብሔር እንዲመርጥልን ጉዳዩን ለእርሱ እንስጥ፡፡ ቀድሞዉኑ እግዚአብሔርን “አንተ የሚሆነውን ቅን መሪ ስጠን” ብለን ሙሉ ፈቃዳችንን ሳንሰጠውና ሳንለምነው እኛው “እንዲህ ቢሆን፣ እገሌ ቢመጣ . . .” እያልን እርሱም ለራሳችን ሃሳብ ከተወን በኋላ የምርጫችንን ስናገኝ እንደገና መልሰን ‘እንዴት እንዲህ ዓይነት ሰው ሰጠኸን?’ ብለን ለመናገር እንዴት እንችላለን?
እግዚአብሔር ይመርጥ ዘንድ አባቶቻችንም እንደ ሐዋርያት በዕጣ ቢያደርጉት መንፈሳዊም ሐዋርያዊ ትወፊትም ነውና ያስመሰግናቸዋል፤ ለማንኛውም ሰው ቢሆን ውጤቱን ለመቀበልም የተመቸ ይሆናል፡፡ የግብፅ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን የፓትርያርክ አመራረጥ ሂደት ላይ መራጮች የሚመርጡት የመጨረሻዎቹ ሦስት ዕጩዎች እስኪቀሩ ድረስ ብቻ ነው፡፡ ከዚያ በኋላ ከሦስቱ አንዱ የሚመረጠው ስማቸው ተጽፎ በመንበር ላይ ይቀመጥና ቅዳሴ ተቀድሶ ሲያበቃ የአምስት ዓመት ሕፃን ልጅ ፊቱ ተሸፍኖ አንድ የተጠቀለለ ወረቀት ያነሣል፣ ወረቀቱ ይገለጥና እዚያ ላይ የተጻፈው ስም አዲሱ ፓትርያርክ ይሆናል፡፡ አሁን ዐቃቤ መንበር ሆነው የተመረጡት ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ጳኩሚስ ደግሞ ይህም ብቻ አይበቃም እያሉ ነው፡፡ ሦስቱንም ዕጩዎች እግዚአብሔር ባይፈልጋቸው በማለት አራተኛ የእግዚአብሔር ሰም የተጻፈበት ወረቀት አብሮ ተጠቅልሎ ሊቀመጥ ይገባል እያሉ ነው፡፡ ይህ በጥንትም በቤቱ ክርስቲያኒቱ በሆነ ዘመን ላይ የነበረ አሠራር ነበር፡፡ የእግዚአብሔር ስም የተጻፈበት ወረቀት ከወጣ ሦስቱንም እግዚአብሔር አልፈለጋቸውም ማለት ስለሆነ ሂደቱ እንደገና ይጀምራል ማለት ነው፡፡
የግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን አባላት በራሳቸው ተመርተው እገሌ ፓትርያርክ ካልሆነ እያሉ የመረጡባቸው ጊዜያት ለቤተ ክርስቲያናቸው እጅግ ከባድ የሆኑ ውድቀቶችን አስከትለውባቸዋል፡፡ ለምሳሌም ከ1946-1956 ዓ.ም. (እኤአ) 115ኛ ፓትርያርክ ተደርገው የተመረጡት አቡነ ዮሳብ ካልአይ በዚህ ዓይነት ሁኔታ የተመረጡ ነበሩ፡፡ ነገር ግን የግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን በፓትርያርኮቿ የአመራር ታሪክ እጅግ በጣም መራር የሚሉት ፈተና የገጠማት በእርሳቸው ዘመን ነበር፡፡ ለቤተ ክርስቲያን የሚሆነውን እረኛ ራሱ እግዚአብሔር እንዲመርጥ ዕድል የሚሰጠውን አሁን ያለውን የፓትርያርክ መምረጫ መስፈርት በ1957 ያወጡት ከዚያ ሁሉ ስህተታቸው በመማር ነበር፡፡ እንዲህ ባለ በመንፈሳዊ መንገድ ሲመርጡ ደግሞ ታላቁን ቅዱስ አባት ቄርሎስ 6ኛን (ከ1959-1971) እና የቅርቡን አቡነ ሺኖዳን (1971-2012) አግኝተዋል፡፡ ስለዚህ ራሳቸው ሲመርጡና እግዚአብሔር እንዲመርጥ ዕድል ሲሰጡ ውጤቱ ምን እንደሆነ በተደጋጋሚ በተግባር አይተውታል፡፡
ስለሆነም በእኛም የፓትርያርክ የምርጫ ሂደት ወደ ምርጫ ከመገባቱ በፊት ከሁሉም አስቀድሞ እንዲህ ዓይነት ለእግዚአብሔር ቦታ የሚሰጥ መንፈሳዊነትና ቀኖናዊነት ያለው የምርጫ ሕግ ሊወጣ ይገባዋል፡፡ በምርጫው ሂደት በአንድ በኩል የተለያየ ዓላማና ፍላጎት ያላቸው ሰዎች እጃቸውን እንዳያስገቡ በመካላከልና በመጠበቅ፣ በሌላ በኩል ደግሞ እግዚአብሔር እንዲመርጥልን የልባችንን በር እንክፈትለት፣ መንገዱንም አንዝጋበት – “አርኁ ኆኃተ መኳንንት ወይባእ ንጉሠ ስብሐት – እናንተ መኳንንት በሮችን ክፈቱ፣ የክብርም ንጉሥ ይግባ” እያለ ይጣራል፡፡ መዝ. 23፡9
2. ምን ጊዜም ለመንፈሳዊነትና ለቀኖናዊነት ቅድሚያውን እንስጥ
ቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊት አካል ናት፣ አካልነቷም የክርስቶስ ነው፡፡ በርግጥ ይህን መንፈሳዊነት ለመጠበቅ አስተዳደራዊና መዋቅራዊ አሠራር የሚያስፈልግ መሆኑ ግልጽ ነው፡፡ ሆኖም ግን ቅድሚያ ሊሰጠው ብቻ ሳይሆን ምን ጊዜም ታላቅ ትኩረት ሊሰጠው የሚገባው ጉዳይ ቤተ ክርስቲያን የቅዱሳን ኅብረት (Communion of Saints) የመሆኗ ነገር ነው፡፡ አንድ የቤተ ክርስቲያን አባት (ፓትርያርክ) በአስተዳደራዊ ችሎታውና አሠራሩ የተዋጣለት ሊሆን ይችላል፣ ነገር ግን መንፈሳዊነት ከተለየው ቤተ ክርስቲያንን እንደ አንድ ዓለማዊ ተቋም ወይም ድርጅት ሊያስመስላት ይችል እንደሆነ እንጂ ቤተ ክርስቲያን አያሰኛትም፤ ቤተ ክርስቲያንን “ቤተ ክርስቲያን” የሚያሰኛት በውስጧ ያለው መዋቅር፣ የሰው ኃይል፣ የገንዘብ መጠን፣ ዓለም አቀፋዊ ግንኙነት፣ . . . ሳይሆን  ከእግዚአብሔርና ከቅዱሳን ጋር ያላት ኅብረትና አንድነት ነው፡፡ እነዚያ አያስፈልጉም ማለት እንዳልሆነ ግልጽ ነው፣ ዋናውና መሠረቱ አይዘንጋ ለማለት እንጂ፡፡
ቤተ ክርስቲያንን በፓትርያርክነት የሚመራ አባት ይቅርና በቅስና ደረጃ ካሉት ጀምሮ በተለያየ ደረጃ ያሉት የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮችና አባቶች በእውቀት ከሌላው ተሽለውና ልቀው መገኘት እንጂ አንሰው ወደ ኋላ መቅረትና ቤተ ክርስቲያንን ማሳፈርና ማስናቅ የለባቸውም፡፡ ከመንፈሳዊው ባሻገር በሳይንሱም በጣም የተማረ የነበረ አንድ የሩሲያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ጳጳስ በአንድ የሳይንቲስቶች የጥናት ጉባኤ ላይ ተገኝቶ ንግግር ሲያደርግ “እስከ ግድግዳው ድረስ ከእናንተ ጋር እኩል እናያለን፣ ከዚያ ባሻገር ያለውንና እናንተ የማታዩትን ደግሞ እኛ ብቻ እናያለን” እንዳለው መናገር የሚችሉ አባቶች ያስፈልጋሉ፡፡ ሆኖም ግን ለቤተ ክርስቲያን አባትነት ዋናው መለኪያ እንዲህ ያለው ዓለማዊ ጥበብና እውቀት አይደለም፡፡ ይህ ሲኖርና ከመንፈሳዊነት ላይ ሲደረብ በእጅጉ የሚጠቅም ሙሉ ጌጥ ይሆናል፡፡ ብቻውን ግን የትም አያደርስም፡፡
አንድ የቤተ ክርስቲያን አባት በቋንቋ ችሎታውና በዲፕሎማሲው ቤተ ክርስቲያንን ከሌላው ዓለም ጋር ማስተዋወቁ መልካም ነገር ነው፡፡ ሆኖም ግን ከእግዚአብሔር ጋር እስካላገናኘንና ከቅዱሳን ጋር ያለውን የመንፈስ አንድነት እስካልጠበቀ ድረስ ከሌሎች መንግሥታትና ድርጅቶች ጋር ስላገናኘን በዚህ ብቻ ቤተ ክርስቲያን ልትጠቀም አትችልም፡፡ ስለዚህ ምን ጊዜም ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባው የቤተ ክርስቲያንን መንፈሳዊነት መጠበቁና ማስጠበቁ ላይ ነው፡፡
እያንዳንዳችንም በመጀመሪያ ከክርስቶስ ጋር አብረን በቤተ ክርስቲያን ሳንሠራና የአካሉ አንድ ክፍል (ብልት) ሳንሆን ስለ አካሉ በማሰብና በመናገር ብቻ ራሳችንንም ቤተ ክርስቲያንንም ልንጠቅም አንችልም፡፡ ጌታችን “እኔ የወይን ግንድ ነኝ፣ እናንተም ቅርንጫፎች ናችሁ” እንዳለ በመጀመሪያ ከግንዱ ያልተቆረጥን ስለመሆናችን እናስብ፡፡ ተቆርጦ የወደቀና ከግንዱ ውጭ የሆነ ክብርና ምስጋና ይግባውና ጌታችን በቅዱስ ቃሉ እንደ ተናገረው “በእኔ የማይኖር ቢሆን እንደ ቅርንጫፍ ወደ ውጭ ይጣላል፣ ይደርቅማል፤ እነርሱንም ሰብስበው ወደ እሳት ይጥሏቸዋል፣ ያቃጥሏቸውማል” ብላል፡፡ በአንጻሩ በእርሱ ለሚኖሩት ደግሞ እንዲህ ይላል፡- “በእኔ ብትኖሩ ቃሎቼም በእናንተ ቢኖሩ የምትወዱትን ሁሉ ለምኑ፤ ይሆንላችሁማል፡፡” ዮሐ. 15፡1-7
ምድራዊ የሆኑ መሥፈርቶችን ዋና ጉዳዮች በማድረግ መሠረታዊ የሆነውን ፈሪሃ እግዚአብሔርን፣ ሃይማኖተኛነትን፣ ቅንነትን፣ ትሑትነትን፣ ወዘተ ችላ በማለት የምናደርገው ነገር እንዳይኖር ወደ ራሳችን መመለስ ያለብን ትክክለኛ ጊዜ ላይ ያለን ይመስላል፡፡ ጌታችን “አስቀድማችሁ የእግዚአብሔርን መንግሥቱንና ጽድቁን ሹ ፈልጉ፣ ሌላው ሁሉ ይጨመርላችኋል” ያለው ለዚህ ነው፡፡ ማቴ. 6፡33 የእግዚአብሔርን መንግሥት፣ ጽድቅን የሚሻ ሰው ወድቆ አይወድቅም፣ ተሻግሮ ያሻግራል፣ ጸሎቱ ይጠቅማል፡፡ በተቃራኒው ምድራዊ የሆነ እውቀት፣ ችሎታ፣ ልምድ፣ . . .  ላይ የምንመሠረት ከሆነ ግን በአሸዋ ላይ እንደ ተሠራው ቤት አንድ ነገር ሲነካው ፈጥኖ ይወድቅና በውስጡ የተጠለሉበትን ሁሉ ጉዳት ያደርስባቸዋል፡፡ ስለሆነም ከውጭ ሰዎች ጋር መነጋገር ስለመቻሉ ሳይሆን ከእግዚአብሔር ጋር በጸሎት መነጋገር ስለመቻሉ፣ ከቅዱሳን ጋር ኅብረት ያለውና እኛንም ወደዚያ የሚመራን ስለመሆኑ ቅድሚያ ሰጥተን እናስብ፡፡ መንፈሳዊ የሆነውን ነገር ስንመኝና ስንፈልግ የልባችንን መሻት የሚያይ እግዚአብሔር እንደ ፈቃዱ የሆነ መሻታችንን ተመልክቶ የተመኘነውን አይነሳንም፡፡ ነገር ግን ምኞታችን ምድራዊና ኃላፊ ጠፊ ስለሆነው ነገር ከሆነ “ወወሀቦሙ ለፍትወቶሙ – እግዚአብሔር ለፈቃዳቸው አሳልፎ ሰጣቸው” እንደ ተባለው ለዚያው ለተመኘነው ነገር አሳልፎ ይሰጠናል፡፡
3. ለቤተ ክርስቲያን የሚጠቅመውን ሃሳብ ብቻ ለመከተል ቁርጥ ሕሊና ይኑረን
ሃሳባችንንና ድርጊታችንን የሚመራው ገዢ ሃሳብ ሐዋርያዊትና ቅድስት ለሆነችው ቤተ ክርስቲያናችን ይጠቅማል ወይስ አይጠቅምም የሚለው እንጂ ግለሰባዊ ወይም ቡድናዊና አካባቢያዊ (ጎጣዊ) ጥቅማ ጥቅም ስሌት ሊሆን አይገባውም፡፡ በእውነቱ ከሆነ እንዲህ ዓይነት አስተሳሰብ ለአንድ ክርስቲያን የሚገባ አይደለም፣ ሃይማኖት ከማጣት የሚመጣ ክፉ ደዌ ነው፡፡ በየጎጡና መንደሩ የምናስብና ሃሳባችን ሁሉ በዚህ የሚቃኝ ከሆነ ስለ አንዲት ቤተ ክርስቲያን በጋራ ማሰብ እንዴት ይቻለናል? ጌታችን “እርስ በርሷ የምትከፋፈል ቤት አትጸናም” በማለት እንደ ነገረን ለሁላችንም የሚጠቅም ነገር ለማግኘት እንዴት አንችላለን?
ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ”ለወገኔ ይጠቅማል በማለት ወይም በከንቱ ውዳሴ ምክንያት አንድ እንኳ አታድርጉ፣ . . .  እያንዳንዱ ለራሱ የሚጠቅመውን አይመልከት፣ ለባልንጀራው ደግሞ እንጂ፡፡ በክርስቶስ ኢየሱስ የነበረ ይህ ሃሳብ በእናንተ ዘንድ ደግሞ ይሁን” በማለት በብርቱ የተማጸነው፡፡ ይህ በሽታ በየትኛውም የሥልጣንም ሆነ የትምህርት ደረጃ ያሉ ሰዎችን ሊጸናወት የሚችል ክፉ ደዌ እንደ ሆነ ስለተረዳ ነው፡፡ ፊል. 2፡3-5 “ለወገኔ ይጠቅማል በማለት ምክንያት አንድ እንኳ አታድርጉ” ሲል አሳሰበን፡፡ እስኪ ይህን የእግዚአብሔር ጽኑ ማሳሰቢያ ስለ እግዚአብሔር ብለን ቆም ብለን እናስተውለው፡፡ ይህ ማለት እያንዳንዱ ለራሱ መንደር ወይም ጎጥ የሚጠቅመውን ብቻ እያሰላ ከዚያ አንጻር የሚሄድ ከሆነ ውጤቱ ብቻ ሳይሆን አስተሳሰቡ በራሱ በቤተ ክርስቲያን አስተምህሮና በአበው ቀኖና የተወገዘ ነው፡፡ እንዲህ የሚያስብ ሰው በቤተ ክርስቲያን አንድነት በሰው ልጅ ወንድማማችነትና እኩልነት የማያምን ነው፡፡ የሚያሳዝነው ግን ይህ ዓይነት አስተሳሰብ ከእኛ ይርቅ ዘንድ በቅዱሳት መጻሕፍት እንዲህ ምክርና ተግሣጽ የተሰጠበት ጉዳይ ቢሆንም በብዙዎቻችን ዘንድ እንደ መልካም ሃሳብ ተቆጥሮ በልቡናችን ተንሰራፍቶና ተደራጅቶ የተቀመጠ መሆኑ ነው፡፡
ከአኃት አብያተ ክርስቲያናት መካከል አንዷ የሆነችው የአርሜንያ ሐዋርያዊት ቤተ ክርስቲያን በ1995 (እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር) በተካሄደው የፓትርያርካቸው ምርጫ ላይ የተካፈሉ መራጮች ከመምረጣቸው በፊት ከዚህ በታች የተመለከተውን ቃለ መሀላ እንዲፈጽሙ ያደረገችው ለዚህ ነበር፡፡ ቃለ መሀላው እንዲህ ይላል፡-
“እኔ ከዚህ በታች የፈረምኩት፣ ካቶሊኮስ (እነርሱ ፓትርያርካቸውን ካቶሊኮስ ነው የሚሉት – ዓለም አቀፋዊ አባት ለማለት) ለመምረጥ በቤ/ክ የተወከልኩት፣ ከፊታችን ባለው የመላዋ አርሜንያውያን ካቶሊኮስ ምርጫ ላይ በጥንቃቄና በማስተዋል፣ ያለ አድልዎ፣ ለቦታው ይሆናል የምለውን ሰው ብቻና ያለ ምንም ግላዊ ፍላጎት፣ እገሌ ቢሆን ከሚል ነገር ራሴን አርቄና ነጻ አድርጌ፣ ከውስጤ ማንኛውንም ዓይነት ክፋትና ተንኮል፣ ጥላቻ፣ ቅናትና ምቀኝነት ወይም የዝምድናም ሆነ የጓደኛነት ትስስር ወይም ቅርበት አርቄ፣ ለክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊ እረኛና ታማኝ የእግዚአብሔር አገልጋይ ይሆናል ብዬ የማስበውን ብቻ የምመርጥ መሆኔን በቅዱስ ወንጌሉ ፊት በኃያሉ በእግዚአብሔር ስም እምላለሁ፡፡
“ተስፋዬ በሆነችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ላይ ቃል እንደ ገባሁት ባላደርግ ግን ራሴን ለመንፈሳውያን ወንድሞቼ ወቀሳ አጋልጣለሁ፣ በዚህም ዓለምም ሆነ በሚመጣው ዓለም በታላቁ የፍርድ ቀን በእግዚአብሔር ፊት እጠየቅበታለሁ፡፡ ቃለ መሀላዬን ለመግለጽ ፍትሐዊ ምርጫ ይሆን ዘንድ የመድኃኒታችንን ቅዱስ ወንጌልና መስቀሉን አስማለሁ፡፡ አሜን፡፡”
አንዳችን ስለ ሁላችን ብናስብ፣ ለአንዲቷ ቤተ ክርስቲያን ስለሚበጀው ብናስብ፣ በጎ ሃሳብን ከምንም ነገር በላይ እንደ ተወደደ መሥዋዕት አድርጎ የሚቀበለው እግዚአብሔር ለሁላችንም የሚጠቅመውን መልካም ነገር ያደርግልናል፡፡ አይሁድ የሰሎሞን ቤተ መቅደስ ስለ ታነጸበት ቦታ እንዲህ የሚል አፈ ታሪክ አላቸው፡፡ ሁለት ወንድማማቾች እርሻቸውን የሚያርሱትና አዝመራውን የሚካፈሉት በጋራ ነበር፡፡ ታላቁ ቤተሰብ ያለው ሲሆን ታናሹ አልነበረውም፡፡ እኩል ከተካፈሉ በኋላ ታናሹ እኔ ብቻዬን ነኝ፣ ወንድሜ ግን ቤተሰብ አለው፣ ስለዚህ እርሱ ከእኔ ይልቅ የበለጠ ያስፈልገዋል እያለ ከእህሉ ከፍሎ ሌሊት ማንም ሳያየው ተሸክሞ እየወሰደ በታላቅ ወንድሙ ጎተራ ይጨምርና ይመለስ ነበር፡፡ ታላቁ ደግሞ ለራሱ እኔ ቤተሰብ መሥርቻለሁ፣ ወንድሜ ግን ገና ብዙ ነገር ይጠብቀዋል፣ ስለዚህ ለእርሱ የበለጠ ያስፈልገዋል እያለ እንዲሁ ሌሊት ተሸክሞ ወስዶ ማንም ሳያየው ከታናሽ ወንድሙ ጎተራ ጨምሮ ይመለስ ነበር፡፡ ሁለቱም ከጎተራቸው ከወሰዱለት በኋላ ጠዋት ሲያዩት ተመልሶ ሞልቶ ስለሚያገኙት ነገሩ ይገርማቸው ነበር፡፡ በእንዲህ ዓይነት ሁኔታ ሲኖሩ አንድ ሌሊት ላይ ታናሹም ተሸክሞ ወደ ታላቁ ጎተራ ሊጨምር ሲሄድ፣ ታላቁም እንዲሁ ወደ ታናሹ ጎተራ ሊጨምር ተሸክሞ ሲሄድ መንገድ ላይ ተገናኙ፡፡ ሁለቱም ሸክማቸውን አውርደው ተቃቅፈው ተላቀሱ፡፡ መሥዋዕት ሲሠዋበትና ሕዝቡ አምልኳቸውን ሲፈጽሙበት የኖሩት የብሉይ ኪዳኑ ቤተ መቅደስ የታነጸበት ቦታ የተሠራው እነዚህ ሁለቱ ወንድማማቾች የተገናኙበት ቦታ ላይ ነው ይላሉ፡፡ እኛ እንዲህ ብንተሳሰብ እግዚአብሔር እርሱ የሚመሰገንበትን እኛም በፍቅር አንድ የምንሆንበትን መንፈስ ይሰጠናል፡፡
ለራሳችንና የእኛ ወገን ለምንለው ብቻ እንድንጠቀም፣ የእኛ ወገን ወይም ቡድን ወይም አካባቢ ብቻ ቀዳሚ ወይም የተለየ ተጠቃሚ እንዲሆን በማስላት የምንሠራው ሥራ ግን ራሳችንንም አይጠቅምም፡፡ ስለሆነም እንኳን በክርስትና ሃይማኖት እኖራለሁ ለሚል ሰው ቀርቶ በፖለቲካ እንኳ እየተጠላ ያለውን እንዲህ ዓይነት አስተሳሰብ እግዚአብሔር ከውስጣችን እንዲያወጣልንና ነጻ እንዲያደርገን እንለምነው፡፡ ለሁላችንም የሚጠቅመወን ለቤተ ክርስቲያን የሚበጀውን በአንድ ልብ ለማሰብ እንሞክር፡፡
4. ወደ እግዚአብሔር እንጸልይ
ነቢዩ ዳዊት “ወከዐው ልበክሙ ቅድሜሁ – ልባችሁን (ሃሳባችሁን፣ ልመናችሁን) በፊቱ አፍሱ (ንገሩት፣ ግለጡለት)” እንዳለ ጸሎት ጭንቀታችንንና ሃሳባችንን ለአባታችን ለእግዚአብሔር የምንገልጥበት ልዩ ሀብት ነው፡፡ ከእኛ በላይ ለእኛ የሚያስፈልገንን የሚያውቅ፣ ከአባታዊ ቸርነቱ የተነሣ የሚጠቅመንን እንጂ የሚጎዳንን የማይሰጥ እርሱን በጸሎት እንጠይቀው፡፡ ድካማችንን የሚያውቅ እርሱ በጸሎት ወደ እርሱ እንደንጠይቀው በቅዱሳት መጻሕፍት በተለያየ መንገድ ደግሞ ደጋግሞ አስተምሮናል፡፡ “ለምኑ፣ ይሰጣችሁማል፤ ፈልጉ፣ ታግኙማላችሁ፤ መዝጊያን አንኳኩ፣ ይከፈትላችሁማል፡፡ የሚለምን ሁሉ ይቀበላልና፣ የሚፈልግም ያገኛል” በማለት ደጋግሞ ካስተማረ በኋላ በምሳሌ ደግሞ እንዲህ አለ፡- “አባት ከሆናችሁ ከእናንተ ከማናችሁም ልጁ እንጀራ ቢለምነው እርሱም ድንጋይ ይሰጠዋልን? ዓሣ ደግሞ ቢለምነው በዓሣ ፋንታ እባብ ይሰጠዋልን? ወይስ እንቁላል ቢለምነው ጊንጥ ይሰጠዋልን? እንኪያስ እናንተ ክፉዎች ስትሆኑ ለልጆቻችሁ መልካም ስጦታ መስጠት ካወቃችሁ በሰማይ ያለው ያለው አባት ለሚለምኑት እንዴት አብልጦ መንፈስ ቅዱስን ይሰጣቸው?” ሉቃ. 11፡9-13
ስለዚህ ብንለምነው የማይሰለቸን፣ ይልቁንም ሳንለምነው ከምንቀር ብንለምነው የሚወድ ቸር አባት እግዚአብሔር እያለን እንዴት የምንሻውን እናጣለን? ሆኖም ስንለምነው ፈቃዱን አውቀን በቅዱሳት መጻሕፍት በታዘዝነው መሠረት ይሆን ዘንድ፣ እንደ ታዘዝነው ለመሆን እንድንችልም ራሳችንን በሚቻለን እያዘጋጀን ሊሆን ይገባል፡፡ እንዲህ ከሆነ ሁሉንም በእኩል ዓይን የሚያይ፣ የወንጌል የመዳን ጸጋ ለሰው ሁሉ እንዲደርስ የሚተጋ፣ በጎቹን በትጋት የሚጠብቅና ስለ አንዲቷ በግ መባዘን ዕረፍት የሚያጣ ደግ እረኛ ይሰጠን ዘንድ ይችላል፡፡
እግዚአብሔር አምላክ “አንብር ለነ ኖላዌ ኄረ ዲበ መንበሩ – በመንበሩ ላይ ቸር እረኛ አስቀምጥልን (አምጣልን)” ብለን የምንጸልየውን ጸሎት ተቀብሎ ቅን መሪ ይስጠን፡፡ አሜን፡፡

(ጸሎተ ኪዳን – ዘሠርክ)

ነሐሴ 18 ቀን 2004 ዓ.ም.

በዲያቆን ያረጋል አበጋዝ

ቤተ ክርስቲያን የምንላት ወልድ ዋሕድ ኢየሱስ ክርስቶስ ከፍጹምና ከማይነገር ፍቅሩ የተነሣ ሰው እስከ መሆን፣ ሰው ሆኖም በዚህ ዓለም ከኃጢአት በስተቀር እንደ ሰው መኖርን፣ ከዚያም በቀራንዮ ቅዱስ ሥጋውን እስኪቆርስላትና ክቡር ደሙን እስኪያፈስላት ድረስ የደረሰላትና የመሠረታት የምእመናን አንድነት (ጉባኤ) ናት፡፡ “ወነአምን በአሐቲ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንተ ላእለ ኩሉ ጉባኤ ዘሐዋርያት” የምንለው ለዚህ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን በወንጌል መሠረትነት በኢየሱስ ክርስቶስ ራስነት በምእመናን አካልነት የተመሠረተች ጉባኤ ናት፡፡

 

 

 

ቤተ ክርስቲያን ስንል የዚህ ዓለም ተጋድሏቸውን በድል አጠናቅቀው ወደ እግዚአብሔር የሄዱ ቅዱሳን (ሐዋርያት፣ ሰማዕታት፣ ሊቃውንት፣ …) እና ገና በዚህ ዓለም በተጋድሎ ላይ ያሉት የምእመናን አንድነት (ጉባኤ) ናት፡፡ በሰማይ ያለችው ቤተ ክርስቲያን (ጉባኤ) የዚህ ዓለም ጣጣቸውን ጨርሰው የሄዱ፣ ድል አድርገው የድል አክሊላቸውን ለመቀበል እርሱ የወሰነውን ጊዜ የሚጠባበቁ ቅዱሳን ኅብረት ስለሆነች አትናወጽም፤ ስለሆነም ሊቃውንት ይህችን ቤተ ክርስቲያን ድል አድራጊዋ ቤተ ክርስቲያን (Church Triumphant) ይሏታል፡፡ ገና በዚህ ዓለም በጉዞና በፈተና ላይ ያለችውን የአንዲቷ ቤተ ክርስቲያን አካል የሆነችውን ጉባኤ (ቤተ ክርስቲያን) ደግሞ ገና በተጋድሎ ላይ ያለች ቤተ ክርስቲያን (Church Militant) ይሏታል፡፡

በዚህ ዓለም ያለችው ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያት በባሕር ላይ በታንኳ እየሄዱ ሳለ ጌታችን አብሯቸው በመካከላቸውና በታንኳው ውስጥ እያለ፣ ነገር ግን በኃይለኛ ማዕበል ትናወጥ እንደ ነበረችው ታንኳ በተለያዩ ፈተናዎች ትናወጻለች፡፡ አንዳንድ ጊዜም በውስጧ ያለው ጌታ የማይሰማና የተዋት፣ መከራዋን እያየ ዝም ያላት፣ ባለቤት የሌላት እስክትመስል ድረስ በውስጧ ያሉና በተለያዩ ነገሮች ተጨንቀው የሚያማርሩና የሚያዝኑ ልጆቿም ሰሚ የሌላቸው የሙት ልጆች እስኪመስሉ ድረስ ባለቤቷ ኢየሱስ ክርስቶስ ዝም ይላል፡፡ ሐዋርያትንም “ስንጠፋ አይገድህምን?” እስኪሉ ያደረሳቸው ይህ ነበር፡፡ ማቴ. 8፡23-27

 

የአንዲቷ ቤተ ክርስቲያን አካል የሆነችው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አምስተኛ ፓትርያርክ የነበሩት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ማረፋቸው ይታወቃል፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን የእርሳቸውን ነፍስ ከቅዱሳን ጋር ይደምርልን እያለች ተተኪውን ስድስተኛውን ፓትርያርክ የመምረጥ ከባድ ሥራ ደግሞ ከፊቷ ተደቅኗል፡፡ ይህ ሥራ ሂደቱና ውጤቱ ቢያንስ ቢያንስ ለሚመጡት የተወሰኑ ዓመታት በቤተ ክርስቲያናችን አካሄድ ላይ የራሱ የሆነ ተጽእኖ የሚኖረው መሆኑ የታወቀ ነው፡፡ የዚህ ጽሑፍ ዓላማም በዚህ ታላቅ ወሳኝ ወቅት ላይ እያንዳንዳችን ምን ብናደርግ እንደሚሻል አጠንክረን እንድናስብ ሕሊናችንን ለማነሣሣት ያህል ነው፡፡

 

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የባለቤቷ የኢየሱስ ክርስቶስ ሙሽራ ስለሆነች ጠባቂዋና ተንከባካቢዋ እርሱ ራሱ ነው፡፡ ምንም እንኳ እርሱ በሚያውቀውና በተለያዩ ምክንያቶች እንድትፈተን ቢፈቅድም እንድትጠፋ ግን አይተዋትም፡፡ ይህ ማለት ግን በውስጧ ያሉ አባላት በጥርጥርና በልዩ ልዩ ፈተናዎች አይሰናከሉም ማለት ግን አይደለም፡፡ ምንም ቢሆን ግን ቤተ ክርስቲያን የራሱ የክርስቶስ አካሉ እንደ መሆኗ ራሷ የሆነ እርሱ ለአካሉ ለምእመናን የሚያስፈልገውን ያውቃል፣ ያዘጋጃል፣ ይሰጣል፡፡ ለዚህ ነው በጸሎተ ኪዳናችን ላይ “ዘይሁብ መርሐ ርቱዐ ለቤተ ክርስቲያን – ለቤተ ክርስቲያን ቅን መሪ የሚሰጥ” የተባለው፡፡

 

ነገር ግን ችግር የሚሆነው ቤተ ክርስቲያን የማን መሆኗን ዘንግተን ባለቤቷና ራሷ የሆነው መድኃኒታችን ኢየሱስ  ክርስቶስ እርሱ ራሱ የሚሆናትን ቅን መሪ እንዲሰጣት ከመጠየቅና ከመማጸን አልፈን እኛው ራሳችን መሪ እንስጥሽ ወደሚል ዝንባሌና አስተሳሰብ ስንሄድ ነው፡፡ እያንዳንዱ ሰው እንደየ እውቀቱና አመለካከቱ ለክርስቶስ ሙሽራ ለሆነችው ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን “እንዲህ ቢሆን፣ እገሌ ቢሆን፣ . . . ” ወደሚል ነገር መምጣት በሽታውን ሳይረዳ እንዲሁ በይመስላል መድኃኒት እንደሚያዝ ሰው መሆን ነው፡፡ በሽታውን ሳይመረምሩና ለመረዳት ጥረት ሳያደርጉ እንዲሁ በግምት፣ በአውቀዋለሁ ባይነትና በግዴለሽነት የሚታዘዘውን እንዲህ ያለውን መድኃኒት መውሰድ ምናልባትም ካለመውሰድ በባሰ ጤናን ሊያውክና ሕማምንም ሊያባብስ ይችላልና፡፡

 

ታዲያ መሥራቿና ባለቤቷ ኢየሱስ ክርስቶስ አካሉ ለሆነችው ለቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ቅን መሪ እንዲሰጣት የእኛ ድርሻ ምን ቢሆን ይሻል ይሆን? ምንስ እናድርግ?

1. መሪ የመስጠቱን ሥራ ለራሱ ለእግዚአብሔር እንስጠው – እኛ ሳንሆን ራሱ ይምረጥልን

እስራኤላውያን ከግብፅ ከወጡ በኋላ መሪያቸውና ንጉሣቸው እግዚአብሔር ሆኖ በተለያዩ መሳፍንት አማካይነት ያስተዳድራቸው ነበር፡፡ መሳፍንቱም የባለ ሥልጣን ወግ ማዕረግ የሌላቸው ከሕዝቡ እንደ አንዱ ሆነው የሚስተዳድሩ፣ ጦርነት ሲሆንና አስፈላጊ በሚሆኑ ዋና ዋና ጉዳዮች ላይ ብቻ የሚመሩ ነበሩ፡፡ ከሙሴ አንስቶ እሰከ ሳሙኤል ዘመን ድረስ ለ450 ዓመታት በዚህ ዓይነት ሁኔታ እየተመሩ ኖሩ፡፡ ሳሙኤልም ምስፍናና ክህነቱን ደርቦ ሕዝቡን አንደ ካህንነቱ ከእግዚአብሔር ጋር እያገናኘ፣ እንደ መሳፍንነቱ ደግሞ አስተዳደራዊ የሆኑ ጉዳዮቹን ያሰዳድራቸው ነበር፡፡ የሐዋ.13፡20-21

እነርሱ በዚህ ሁኔታ እየኖሩ ሳለ በአካባቢያቸው የሚኖሩ የተለያዩ አሕዛብ ደግሞ የራሱ የሆነ የንግሥና ሥርዓት፣ አፋሽ አጎንባሽ፣ ሠረገላና ሠራዊት፣ ሽቶ ቀማሚዎች፣ ወጥ ቤቶችና እንጀራ አበዛዎች ያሏቸው፣ ሕዝቡን የሚያስገብሩ ነገሥታት ነበሯቸው፡፡ እስራኤላውያን በአሕዛብ በመቅናት ንጉሣቸው እግዚአብሔር መሆኑ ቀርቶ እንደ ሌሎቹ ጎረቤቶቻቸው ከመካከላቸው አንዱን እነዲያነግሥላቸው በሳሙኤል በኩል ጠየቁ፡፡ በዚህ ጊዜ ሳሙኤል ወደ እግዚአብሔር ጸለየ፡፡ እግዚአብሔርም ሳሙኤልን አለው፡-

 

“በእነርሱ ላይ እንዳልነግሥ እኔን እንጂ አንተን አልናቁምና በሚሉህ ነገር ሁሉ የሕዝቡን ቃል ስማ፡፡ ከግብጽ ካወጣኋቸው ቀን ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ እኔን ትተው እንግዶች አማልክት በማምለካቸው እንደ ሠሩት ሥራ ሁሉ እንዲሁ በአንተ ደግሞ ያደርጉብሃል፡፡ . . . ለሕዝቡም በእናንተ ላይ የሚነግሠው የንጉሡ ወግ ይህ ነው ብለህ ንገራቸው፡- ወንዶች ልጆቻችሁን ወስዶ ሰረገለኞችና ፈረሰኞች ያደርጋቸዋል፣ . . . ሎሌዎቻችሁንና ገረዶቻችሁን ከከብቶቻችሁና ከአህዮቻችሁም መካከል መልካሞቹን ወስዶ ያሠራቸዋል፡፡ ከበጎቻችሁና ከፍየሎቻችሁ አሥራት ይወስዳል፤ እናንተም ባሪያዎች ትሆኑታላችሁ፡፡ በዚያም ቀን ለእናንተ ከመረጣችሁት ከንጉሣችሁ የተነሣ ትጮኻላችሁ፤ በዚያም ቀን እግዚአብሔር አይሰማችሁም፡፡” 1 ሳሙ. 8፡10-18

 

እንደ ልመናቸው ንጉሥ ሰጣቸው፣ ሳኦልን አነገሠላቸው፡፡ ሆኖም እግዚአብሔር አስቀድሞ እንደ ነገራቸው ብዙም ሳይቆይ ንጉሦቻቸው ለሕዝበ እስራኤል ዋናው የጥፋታቸው መሪዎች በመሆን የጥፋታቸውን ጎዳና ደኅና አድርገው ጠርገውላቸዋል፡፡ በንጉሥ ሰሎሞን ኃጢአት ምክንያት በልጁ በሮብአም ዘመን አንድ የነበረው ሕዝብ ከሁለት ተከፈለ፤ አሥሩ ነገድ የእስራኤል መንግሥት ተብሎ በሰሜን፣ ሁለቱ ነገድ ደግሞ በደቡብ የይሁዳ መንግሥት ተብሎ በ928 ቅድመ ልደተ ክርስቶስ ዳግመኛ አንድ ላይሆኑ ተለያዩ፡፡

 

ቀጥሎም የአሥሩ ነገድ ንጉሥ የነበረው ኢዮርብዓም በግዛታቸው በስሜንና በደቡብ ጫፍ ላይ በዳንና በቤቴል ጣዖት አቁሞ ከዚያ በፊት ይደረግ እንደ ነበረው ሕዝቡ ወደ ኢየሩሳሌም ሄዶ በታቦተ ጽዮን ፊት በቤተ መቅደሱ መሥዋዕት አቅርቦ አምላኩን እግዚአብሔርን አዘክሮ እንዳይመለስ በዚያው በሰሜኑ ግዛት ብቻ ተገድቦ እንዲቀር ለማድረግ ሲል ባቆማቸው ጣዖታት ሕዝቡን እግዚአብሔርን ከማምለክ ጣዖት ወደ ማምለክ እንዲያዘነብል አደረገው፡፡ ከዚሁም ጋር ንጉሣቸው ኢዮርብዓም እንደ ሕጉ መሠረት ካህናትን ከሌዋውያን ሳይሆን ሌዋውያን ካልሆኑት መካከል ለራሱ የሚመቹትን ካህናት ናቸው ብሎ መረጠ፣ በዓል የሚከበርበትን ቀን ለወጠ፣ በአጠቃላይ በኦሪቱ የተሰጠውን ነገር ሁሉ ገለባበጠው፡፡

 

እስራኤላውያን አስቀድሞ የንጉሥ አንግሥልን ምርጫቸው ምን እንደሚያስከትል በግልጽ እንደ ተነገራቸው ሆነባቸው፡፡ የሰሜኑ ግዛት የአሥሩ ነገድ ነገሥታት ኢዮርብዓም በጀመረው ከእግዚአብሔር የመለየትና ጣዖት የማምለክ የጥፋት ጎዳና እየገፉበት ሄዱ፡፡ ከዚያም በኋላ እነ አክአብና ኤልዛቤል ክህደቱና ኃጢአቱ፣ ግፉና ዓመጹ መሥፈሪያውን ቶሎ እንዲሞላ እያቻኮለው ሄደ፡፡ በዚያ የጥፋት ቁልቁሊት በፍጥነት በመቀጠል የእስራኤል መንግሥት ለሁለት በተከፈለ በ210 ዓመት (በ718 ቅድመ ልደተ ክርስቶስ) በአሶራውያን ተማርከው ተወሰዱ፡፡ 2 ነገ. ምዕ. 17 ከዚያ በኋላ የአሥሩ ነገድ ነገር የውኃ ሽታ ሆኖ ቀረ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ስለ አሥሩ ነገድ መማረክ ይነግረናል እንጂ ከዚያ በኋላ የት እንደ ደረሱና ምን እንደ ሆኑ አይነግረንም፡፡ በመጽሐፈ ዕዝራና ነህምያ ከምርኮ ስለ መመለሳቸው የተጻፈላቸው በኋላ የተማረኩት ሁለቱ ነገድ ናቸው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ከተነገሩና ምሥጢራቸው ካልተፈታ ታሪኮች አንዱ ይህ የአሥሩ ነገድ ጉዳይ ነው፡፡ እንግዲህ ያ የወደዱትና ጓጉተውና ሽተው የለመኑት የንጉሥ አንግሥልን ጥያቄ ነገር ፍጻሜያቸው እንዲህ አሳዛኝ እንዲሆን አድርጎታል፡፡

 

በዚሁ ንጉሥ የማንገሥ ጉዳይ ነቢዩ ሳሙኤል ከእግዚአብሔር ፊት በተናቀው በሳኦል ፋንታ የሚቀባውን ሊፈልግ ወደ ቤተ ልሔም ሄዶ ወደ እሴይ ቤት ገብቶ በዚያ የነበሩትን የእሴይን ልጆች ተራ በተራ ሲያልፉ ዓይኑ ኤልያብ ላይ አርፎ ነበር፡፡ ኤልያብ በሰው አስተሳሰብ መልከ መልካምና ተክለ ቁመናው የሚስብ ስለነበር ነቢዩ ሳሙኤል እርሱን ሲመለከት “በእውነት እግዚአብሔር የሚቀባው በፊቱ ነው” አለ፡፡ እግዚአብሔር ግን ሳሙኤልን፡- “ፊቱን የቁመቱንም ዘለግታ አትይ፤ ሰው እንዲያይ እግዚአብሔር አያይምና ናቅሁት፤ ሰው ፊትን ያያል፣ እግዚአብሔር ግን ልብን ያያል” አለው፡፡ ሌሎቹም የእሴይ ልጆች እነ አሚናዳብ፣ ሣማን፣ … በፊቱ አለፉ፡፡ ሆኖም እነዚያ ሁሉም “ይህን ደግሞ እግዚአብሔር አልመረጠውም” እየተባሉ በፊቱ አለፉ፡፡ እግዚአብሔር የመረጠው አባቱ እንኳ ሳይቀር ለዚህ ይሆናል ብሎ ያላሳበው፣ ከዚህም የተነሣ ከመሥዋዕቱ ጥሪና ከበዓሉ ሥርዓት ለይቶ በጎችን እንዲጠብቅ በዱር የተወው ዳዊት ነበር፡፡

 

የሰው የምርጫ መለኪያና የእግዚአብሔር የምርጫ መለኪያ ምን ያህል የተራራቁና የተለያዩ እንደ ሆኑ እናስተውል፡፡ ሌላው ቀርቶ ክህነት ከምስፍና ደርቦ የያዘው ታላቁ ነቢይ ሳሙኤል እንኳ ኤልያብን ሲያየው ገጽታውን በመመልከት ብቻ ወዲያዉኑ ደስ ብሎት “በእውነት እግዚአብሔር የሚቀባው በፊቱ ነው” እስኪል ያደረሰው በውጫዊ ነገር በመሳቡና በመመሰጡ ነበር፡፡ እግዚአብሔር በዚህ ጊዜ “ኢትርአይ ግርማ ርእየቱ ለኤልያብ – የኤልያብን ፊቱን የቁመቱንም ዘለግታ አትይ” የሚል ተግሣጽ አከል ነገር የተናገረው ለዚህ ነበር፡፡ እንግዲህ እንዲህ ያሉ ታላላቅ አባቶች እንኳ እግዚአብሔር ያዘጋጀውንና የመረጠውን ለማወቅ ይህን ያህል የሚቸገሩና ለዚህ ጥሪ የማይሆኑ ብዙ ሰዎችን አጣርተው (በፊታቸው አሳልፈው) መተው ያለባቸው ከሆነ ለእኛማ ምን ያህል ከባድ ይሆን?

ይህ ማለት እኛ መሥራት ያለብንን ሥራ መሥራት የለብንም ማለት አይደለም፡፡ ነገር ግን እንዲህ ዓይነት ቤተ ክርስቲያንን በአባትነት የሚመራ፣ ለመንጋው ታማኝ የሆነና መንጋውም የሚወደውና የሚያፈቅረው፣ ምንደኛ ያይደለ እረኛ፣ ጌታ ሳይሆን አገልጋይ፣ ለራሱ ሥልጣንና ክብር ሳይሆን ለእግዚአብሔር ክብር የሚቀና፣ ውስብስብ የሆነውን ዓለም በመስቀል ተደግፎ የሚሻገርና የሚያሻግር፣ ቤተ ክርስቲያንን የሚመራ፣ ራሱ ግን በእግዚአብሔር የሚመራ ሰው ማግኘት ለሰው ከባድ ስለሆነ ነው ሁሉን ለሚያውቀው ለእርሱ መተው ከሁሉም የተሻለ አማራጭ የሚሆነው፡፡ ራሱ ባለቤቱም ይህን ሲያስተምረን “መኑ እንጋ ገብር ምእምን ወጠቢብ ዘይሠይሞ እግዚኡ ውስተ ኩሉ ቤቱ ከመ የሀቦሙ ሲሳዮሙ በጊዜሁ – ምግባቸውን በየጊዜው ይሰጣቸው ዘንድ ጌታው በቤተ ሰዎቹ ላይ የሚሾመው ልባምና ታማኝ ባሪያ ማን ነው?” ሲል የጠየቀው እንዲህ ያሉ ታማኝ አገልጋዮችን (ጌቶችን አላለም) ማግኘት ምን ያህል ከባድ እንደሆነ ሲያስተምረን ነው፡፡ ማቴ. 24፡45

ቅዱሳን ሐዋርያት በይሁዳ ቦታ የሚተካና ከአሥራ ሁለቱ ሐዋርያት ገብቶ የሚቆጠር ሰው ሊመርጡ ሲሉ ሁለት ሰዎችን አቀረቡና ከሁለቱ አንዱን እግዚአብሔር እንዲመርጥላቸው ዕጣ ጣሉ፡፡ ዕጣውም ለማትያስ ወደቀ፡፡ ታዲያ ሐዋርያት እንዲህ ምርጫውን ለእግዚአብሔር ከሰጡ እኛ ለእርሱ የማንሰጥበት ምክንያት ምን ይሆን? የሐዋ. 1፡21-26

 

ስለሆነም እኛ እያንዳንዳችን እግዚአብሔር እንዲመርጥልን ጉዳዩን ለእርሱ እንስጥ፡፡ ቀድሞዉኑ እግዚአብሔርን “አንተ የሚሆነውን ቅን መሪ ስጠን” ብለን ሙሉ ፈቃዳችንን ሳንሰጠውና ሳንለምነው እኛው “እንዲህ ቢሆን፣ እገሌ ቢመጣ . . .” እያልን እርሱም ለራሳችን ሃሳብ ከተወን በኋላ የምርጫችንን ስናገኝ እንደገና መልሰን ‘እንዴት እንዲህ ዓይነት ሰው ሰጠኸን?’ ብለን ለመናገር እንዴት እንችላለን?

 

እግዚአብሔር ይመርጥ ዘንድ አባቶቻችንም እንደ ሐዋርያት በዕጣ ቢያደርጉት መንፈሳዊም ሐዋርያዊ ትወፊትም ነውና ያስመሰግናቸዋል፤ ለማንኛውም ሰው ቢሆን ውጤቱን ለመቀበልም የተመቸ ይሆናል፡፡ የግብፅ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን የፓትርያርክ አመራረጥ ሂደት ላይ መራጮች የሚመርጡት የመጨረሻዎቹ ሦስት ዕጩዎች እስኪቀሩ ድረስ ብቻ ነው፡፡ ከዚያ በኋላ ከሦስቱ አንዱ የሚመረጠው ስማቸው ተጽፎ በመንበር ላይ ይቀመጥና ቅዳሴ ተቀድሶ ሲያበቃ የአምስት ዓመት ሕፃን ልጅ ፊቱ ተሸፍኖ አንድ የተጠቀለለ ወረቀት ያነሣል፣ ወረቀቱ ይገለጥና እዚያ ላይ የተጻፈው ስም አዲሱ ፓትርያርክ ይሆናል፡፡ አሁን ዐቃቤ መንበር ሆነው የተመረጡት ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ጳኩሚስ ደግሞ ይህም ብቻ አይበቃም እያሉ ነው፡፡ ሦስቱንም ዕጩዎች እግዚአብሔር ባይፈልጋቸው በማለት አራተኛ የእግዚአብሔር ሰም የተጻፈበት ወረቀት አብሮ ተጠቅልሎ ሊቀመጥ ይገባል እያሉ ነው፡፡ ይህ በጥንትም በቤቱ ክርስቲያኒቱ በሆነ ዘመን ላይ የነበረ አሠራር ነበር፡፡ የእግዚአብሔር ስም የተጻፈበት ወረቀት ከወጣ ሦስቱንም እግዚአብሔር አልፈለጋቸውም ማለት ስለሆነ ሂደቱ እንደገና ይጀምራል ማለት ነው፡፡

 

የግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን አባላት በራሳቸው ተመርተው እገሌ ፓትርያርክ ካልሆነ እያሉ የመረጡባቸው ጊዜያት ለቤተ ክርስቲያናቸው እጅግ ከባድ የሆኑ ውድቀቶችን አስከትለውባቸዋል፡፡ ለምሳሌም ከ1946-1956 ዓ.ም. (እኤአ) 115ኛ ፓትርያርክ ተደርገው የተመረጡት አቡነ ዮሳብ ካልአይ በዚህ ዓይነት ሁኔታ የተመረጡ ነበሩ፡፡ ነገር ግን የግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን በፓትርያርኮቿ የአመራር ታሪክ እጅግ በጣም መራር የሚሉት ፈተና የገጠማት በእርሳቸው ዘመን ነበር፡፡ ለቤተ ክርስቲያን የሚሆነውን እረኛ ራሱ እግዚአብሔር እንዲመርጥ ዕድል የሚሰጠውን አሁን ያለውን የፓትርያርክ መምረጫ መስፈርት በ1957 ያወጡት ከዚያ ሁሉ ስህተታቸው በመማር ነበር፡፡ እንዲህ ባለ በመንፈሳዊ መንገድ ሲመርጡ ደግሞ ታላቁን ቅዱስ አባት ቄርሎስ 6ኛን (ከ1959-1971) እና የቅርቡን አቡነ ሺኖዳን (1971-2012) አግኝተዋል፡፡ ስለዚህ ራሳቸው ሲመርጡና እግዚአብሔር እንዲመርጥ ዕድል ሲሰጡ ውጤቱ ምን እንደሆነ በተደጋጋሚ በተግባር አይተውታል፡፡

 

ስለሆነም በእኛም የፓትርያርክ የምርጫ ሂደት ወደ ምርጫ ከመገባቱ በፊት ከሁሉም አስቀድሞ እንዲህ ዓይነት ለእግዚአብሔር ቦታ የሚሰጥ መንፈሳዊነትና ቀኖናዊነት ያለው የምርጫ ሕግ ሊወጣ ይገባዋል፡፡ በምርጫው ሂደት በአንድ በኩል የተለያየ ዓላማና ፍላጎት ያላቸው ሰዎች እጃቸውን እንዳያስገቡ በመካላከልና በመጠበቅ፣ በሌላ በኩል ደግሞ እግዚአብሔር እንዲመርጥልን የልባችንን በር እንክፈትለት፣ መንገዱንም አንዝጋበት – “አርኁ ኆኃተ መኳንንት ወይባእ ንጉሠ ስብሐት – እናንተ መኳንንት በሮችን ክፈቱ፣ የክብርም ንጉሥ ይግባ” እያለ ይጣራል፡፡ መዝ. 23፡9

2. ምን ጊዜም ለመንፈሳዊነትና ለቀኖናዊነት ቅድሚያውን እንስጥ

ቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊት አካል ናት፣ አካልነቷም የክርስቶስ ነው፡፡ በርግጥ ይህን መንፈሳዊነት ለመጠበቅ አስተዳደራዊና መዋቅራዊ አሠራር የሚያስፈልግ መሆኑ ግልጽ ነው፡፡ ሆኖም ግን ቅድሚያ ሊሰጠው ብቻ ሳይሆን ምን ጊዜም ታላቅ ትኩረት ሊሰጠው የሚገባው ጉዳይ ቤተ ክርስቲያን የቅዱሳን ኅብረት (Communion of Saints) የመሆኗ ነገር ነው፡፡ አንድ የቤተ ክርስቲያን አባት (ፓትርያርክ) በአስተዳደራዊ ችሎታውና አሠራሩ የተዋጣለት ሊሆን ይችላል፣ ነገር ግን መንፈሳዊነት ከተለየው ቤተ ክርስቲያንን እንደ አንድ ዓለማዊ ተቋም ወይም ድርጅት ሊያስመስላት ይችል እንደሆነ እንጂ ቤተ ክርስቲያን አያሰኛትም፤ ቤተ ክርስቲያንን “ቤተ ክርስቲያን” የሚያሰኛት በውስጧ ያለው መዋቅር፣ የሰው ኃይል፣ የገንዘብ መጠን፣ ዓለም አቀፋዊ ግንኙነት፣ . . . ሳይሆን  ከእግዚአብሔርና ከቅዱሳን ጋር ያላት ኅብረትና አንድነት ነው፡፡ እነዚያ አያስፈልጉም ማለት እንዳልሆነ ግልጽ ነው፣ ዋናውና መሠረቱ አይዘንጋ ለማለት እንጂ፡፡

 

ቤተ ክርስቲያንን በፓትርያርክነት የሚመራ አባት ይቅርና በቅስና ደረጃ ካሉት ጀምሮ በተለያየ ደረጃ ያሉት የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮችና አባቶች በእውቀት ከሌላው ተሽለውና ልቀው መገኘት እንጂ አንሰው ወደ ኋላ መቅረትና ቤተ ክርስቲያንን ማሳፈርና ማስናቅ የለባቸውም፡፡ ከመንፈሳዊው ባሻገር በሳይንሱም በጣም የተማረ የነበረ አንድ የሩሲያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ጳጳስ በአንድ የሳይንቲስቶች የጥናት ጉባኤ ላይ ተገኝቶ ንግግር ሲያደርግ “እስከ ግድግዳው ድረስ ከእናንተ ጋር እኩል እናያለን፣ ከዚያ ባሻገር ያለውንና እናንተ የማታዩትን ደግሞ እኛ ብቻ እናያለን” እንዳለው መናገር የሚችሉ አባቶች ያስፈልጋሉ፡፡ ሆኖም ግን ለቤተ ክርስቲያን አባትነት ዋናው መለኪያ እንዲህ ያለው ዓለማዊ ጥበብና እውቀት አይደለም፡፡ ይህ ሲኖርና ከመንፈሳዊነት ላይ ሲደረብ በእጅጉ የሚጠቅም ሙሉ ጌጥ ይሆናል፡፡ ብቻውን ግን የትም አያደርስም፡፡

 

አንድ የቤተ ክርስቲያን አባት በቋንቋ ችሎታውና በዲፕሎማሲው ቤተ ክርስቲያንን ከሌላው ዓለም ጋር ማስተዋወቁ መልካም ነገር ነው፡፡ ሆኖም ግን ከእግዚአብሔር ጋር እስካላገናኘንና ከቅዱሳን ጋር ያለውን የመንፈስ አንድነት እስካልጠበቀ ድረስ ከሌሎች መንግሥታትና ድርጅቶች ጋር ስላገናኘን በዚህ ብቻ ቤተ ክርስቲያን ልትጠቀም አትችልም፡፡ ስለዚህ ምን ጊዜም ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባው የቤተ ክርስቲያንን መንፈሳዊነት መጠበቁና ማስጠበቁ ላይ ነው፡፡

 

እያንዳንዳችንም በመጀመሪያ ከክርስቶስ ጋር አብረን በቤተ ክርስቲያን ሳንሠራና የአካሉ አንድ ክፍል (ብልት) ሳንሆን ስለ አካሉ በማሰብና በመናገር ብቻ ራሳችንንም ቤተ ክርስቲያንንም ልንጠቅም አንችልም፡፡ ጌታችን “እኔ የወይን ግንድ ነኝ፣ እናንተም ቅርንጫፎች ናችሁ” እንዳለ በመጀመሪያ ከግንዱ ያልተቆረጥን ስለመሆናችን እናስብ፡፡ ተቆርጦ የወደቀና ከግንዱ ውጭ የሆነ ክብርና ምስጋና ይግባውና ጌታችን በቅዱስ ቃሉ እንደ ተናገረው “በእኔ የማይኖር ቢሆን እንደ ቅርንጫፍ ወደ ውጭ ይጣላል፣ ይደርቅማል፤ እነርሱንም ሰብስበው ወደ እሳት ይጥሏቸዋል፣ ያቃጥሏቸውማል” ብላል፡፡ በአንጻሩ በእርሱ ለሚኖሩት ደግሞ እንዲህ ይላል፡- “በእኔ ብትኖሩ ቃሎቼም በእናንተ ቢኖሩ የምትወዱትን ሁሉ ለምኑ፤ ይሆንላችሁማል፡፡” ዮሐ. 15፡1-7

 

ምድራዊ የሆኑ መሥፈርቶችን ዋና ጉዳዮች በማድረግ መሠረታዊ የሆነውን ፈሪሃ እግዚአብሔርን፣ ሃይማኖተኛነትን፣ ቅንነትን፣ ትሑትነትን፣ ወዘተ ችላ በማለት የምናደርገው ነገር እንዳይኖር ወደ ራሳችን መመለስ ያለብን ትክክለኛ ጊዜ ላይ ያለን ይመስላል፡፡ ጌታችን “አስቀድማችሁ የእግዚአብሔርን መንግሥቱንና ጽድቁን ሹ ፈልጉ፣ ሌላው ሁሉ ይጨመርላችኋል” ያለው ለዚህ ነው፡፡ ማቴ. 6፡33 የእግዚአብሔርን መንግሥት፣ ጽድቅን የሚሻ ሰው ወድቆ አይወድቅም፣ ተሻግሮ ያሻግራል፣ ጸሎቱ ይጠቅማል፡፡ በተቃራኒው ምድራዊ የሆነ እውቀት፣ ችሎታ፣ ልምድ፣ . . .  ላይ የምንመሠረት ከሆነ ግን በአሸዋ ላይ እንደ ተሠራው ቤት አንድ ነገር ሲነካው ፈጥኖ ይወድቅና በውስጡ የተጠለሉበትን ሁሉ ጉዳት ያደርስባቸዋል፡፡ ስለሆነም ከውጭ ሰዎች ጋር መነጋገር ስለመቻሉ ሳይሆን ከእግዚአብሔር ጋር በጸሎት መነጋገር ስለመቻሉ፣ ከቅዱሳን ጋር ኅብረት ያለውና እኛንም ወደዚያ የሚመራን ስለመሆኑ ቅድሚያ ሰጥተን እናስብ፡፡ መንፈሳዊ የሆነውን ነገር ስንመኝና ስንፈልግ የልባችንን መሻት የሚያይ እግዚአብሔር እንደ ፈቃዱ የሆነ መሻታችንን ተመልክቶ የተመኘነውን አይነሳንም፡፡ ነገር ግን ምኞታችን ምድራዊና ኃላፊ ጠፊ ስለሆነው ነገር ከሆነ “ወወሀቦሙ ለፍትወቶሙ – እግዚአብሔር ለፈቃዳቸው አሳልፎ ሰጣቸው” እንደ ተባለው ለዚያው ለተመኘነው ነገር አሳልፎ ይሰጠናል፡፡

 

3. ለቤተ ክርስቲያን የሚጠቅመውን ሃሳብ ብቻ ለመከተል ቁርጥ ሕሊና ይኑረን

ሃሳባችንንና ድርጊታችንን የሚመራው ገዢ ሃሳብ ሐዋርያዊትና ቅድስት ለሆነችው ቤተ ክርስቲያናችን ይጠቅማል ወይስ አይጠቅምም የሚለው እንጂ ግለሰባዊ ወይም ቡድናዊና አካባቢያዊ (ጎጣዊ) ጥቅማ ጥቅም ስሌት ሊሆን አይገባውም፡፡ በእውነቱ ከሆነ እንዲህ ዓይነት አስተሳሰብ ለአንድ ክርስቲያን የሚገባ አይደለም፣ ሃይማኖት ከማጣት የሚመጣ ክፉ ደዌ ነው፡፡ በየጎጡና መንደሩ የምናስብና ሃሳባችን ሁሉ በዚህ የሚቃኝ ከሆነ ስለ አንዲት ቤተ ክርስቲያን በጋራ ማሰብ እንዴት ይቻለናል? ጌታችን “እርስ በርሷ የምትከፋፈል ቤት አትጸናም” በማለት እንደ ነገረን ለሁላችንም የሚጠቅም ነገር ለማግኘት እንዴት አንችላለን?

 

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ”ለወገኔ ይጠቅማል በማለት ወይም በከንቱ ውዳሴ ምክንያት አንድ እንኳ አታድርጉ፣ . . .  እያንዳንዱ ለራሱ የሚጠቅመውን አይመልከት፣ ለባልንጀራው ደግሞ እንጂ፡፡ በክርስቶስ ኢየሱስ የነበረ ይህ ሃሳብ በእናንተ ዘንድ ደግሞ ይሁን” በማለት በብርቱ የተማጸነው፡፡ ይህ በሽታ በየትኛውም የሥልጣንም ሆነ የትምህርት ደረጃ ያሉ ሰዎችን ሊጸናወት የሚችል ክፉ ደዌ እንደ ሆነ ስለተረዳ ነው፡፡ ፊል. 2፡3-5 “ለወገኔ ይጠቅማል በማለት ምክንያት አንድ እንኳ አታድርጉ” ሲል አሳሰበን፡፡ እስኪ ይህን የእግዚአብሔር ጽኑ ማሳሰቢያ ስለ እግዚአብሔር ብለን ቆም ብለን እናስተውለው፡፡ ይህ ማለት እያንዳንዱ ለራሱ መንደር ወይም ጎጥ የሚጠቅመውን ብቻ እያሰላ ከዚያ አንጻር የሚሄድ ከሆነ ውጤቱ ብቻ ሳይሆን አስተሳሰቡ በራሱ በቤተ ክርስቲያን አስተምህሮና በአበው ቀኖና የተወገዘ ነው፡፡ እንዲህ የሚያስብ ሰው በቤተ ክርስቲያን አንድነት በሰው ልጅ ወንድማማችነትና እኩልነት የማያምን ነው፡፡ የሚያሳዝነው ግን ይህ ዓይነት አስተሳሰብ ከእኛ ይርቅ ዘንድ በቅዱሳት መጻሕፍት እንዲህ ምክርና ተግሣጽ የተሰጠበት ጉዳይ ቢሆንም በብዙዎቻችን ዘንድ እንደ መልካም ሃሳብ ተቆጥሮ በልቡናችን ተንሰራፍቶና ተደራጅቶ የተቀመጠ መሆኑ ነው፡፡

 

ከአኃት አብያተ ክርስቲያናት መካከል አንዷ የሆነችው የአርሜንያ ሐዋርያዊት ቤተ ክርስቲያን በ1995 (እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር) በተካሄደው የፓትርያርካቸው ምርጫ ላይ የተካፈሉ መራጮች ከመምረጣቸው በፊት ከዚህ በታች የተመለከተውን ቃለ መሀላ እንዲፈጽሙ ያደረገችው ለዚህ ነበር፡፡ ቃለ መሀላው እንዲህ ይላል፡-

 

“እኔ ከዚህ በታች የፈረምኩት፣ ካቶሊኮስ (እነርሱ ፓትርያርካቸውን ካቶሊኮስ ነው የሚሉት – ዓለም አቀፋዊ አባት ለማለት) ለመምረጥ በቤ/ክ የተወከልኩት፣ ከፊታችን ባለው የመላዋ አርሜንያውያን ካቶሊኮስ ምርጫ ላይ በጥንቃቄና በማስተዋል፣ ያለ አድልዎ፣ ለቦታው ይሆናል የምለውን ሰው ብቻና ያለ ምንም ግላዊ ፍላጎት፣ እገሌ ቢሆን ከሚል ነገር ራሴን አርቄና ነጻ አድርጌ፣ ከውስጤ ማንኛውንም ዓይነት ክፋትና ተንኮል፣ ጥላቻ፣ ቅናትና ምቀኝነት ወይም የዝምድናም ሆነ የጓደኛነት ትስስር ወይም ቅርበት አርቄ፣ ለክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊ እረኛና ታማኝ የእግዚአብሔር አገልጋይ ይሆናል ብዬ የማስበውን ብቻ የምመርጥ መሆኔን በቅዱስ ወንጌሉ ፊት በኃያሉ በእግዚአብሔር ስም እምላለሁ፡፡ “ተስፋዬ በሆነችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ላይ ቃል እንደ ገባሁት ባላደርግ ግን ራሴን ለመንፈሳውያን ወንድሞቼ ወቀሳ አጋልጣለሁ፣ በዚህም ዓለምም ሆነ በሚመጣው ዓለም በታላቁ የፍርድ ቀን በእግዚአብሔር ፊት እጠየቅበታለሁ፡፡ ቃለ መሀላዬን ለመግለጽ ፍትሐዊ ምርጫ ይሆን ዘንድ የመድኃኒታችንን ቅዱስ ወንጌልና መስቀሉን አስማለሁ፡፡ አሜን፡፡”


አንዳችን ስለ ሁላችን ብናስብ፣ ለአንዲቷ ቤተ ክርስቲያን ስለሚበጀው ብናስብ፣ በጎ ሃሳብን ከምንም ነገር በላይ እንደ ተወደደ መሥዋዕት አድርጎ የሚቀበለው እግዚአብሔር ለሁላችንም የሚጠቅመውን መልካም ነገር ያደርግልናል፡፡ አይሁድ የሰሎሞን ቤተ መቅደስ ስለ ታነጸበት ቦታ እንዲህ የሚል አፈ ታሪክ አላቸው፡፡ ሁለት ወንድማማቾች እርሻቸውን የሚያርሱትና አዝመራውን የሚካፈሉት በጋራ ነበር፡፡ ታላቁ ቤተሰብ ያለው ሲሆን ታናሹ አልነበረውም፡፡ እኩል ከተካፈሉ በኋላ ታናሹ እኔ ብቻዬን ነኝ፣ ወንድሜ ግን ቤተሰብ አለው፣ ስለዚህ እርሱ ከእኔ ይልቅ የበለጠ ያስፈልገዋል እያለ ከእህሉ ከፍሎ ሌሊት ማንም ሳያየው ተሸክሞ እየወሰደ በታላቅ ወንድሙ ጎተራ ይጨምርና ይመለስ ነበር፡፡ ታላቁ ደግሞ ለራሱ እኔ ቤተሰብ መሥርቻለሁ፣ ወንድሜ ግን ገና ብዙ ነገር ይጠብቀዋል፣ ስለዚህ ለእርሱ የበለጠ ያስፈልገዋል እያለ እንዲሁ ሌሊት ተሸክሞ ወስዶ ማንም ሳያየው ከታናሽ ወንድሙ ጎተራ ጨምሮ ይመለስ ነበር፡፡ ሁለቱም ከጎተራቸው ከወሰዱለት በኋላ ጠዋት ሲያዩት ተመልሶ ሞልቶ ስለሚያገኙት ነገሩ ይገርማቸው ነበር፡፡ በእንዲህ ዓይነት ሁኔታ ሲኖሩ አንድ ሌሊት ላይ ታናሹም ተሸክሞ ወደ ታላቁ ጎተራ ሊጨምር ሲሄድ፣ ታላቁም እንዲሁ ወደ ታናሹ ጎተራ ሊጨምር ተሸክሞ ሲሄድ መንገድ ላይ ተገናኙ፡፡ ሁለቱም ሸክማቸውን አውርደው ተቃቅፈው ተላቀሱ፡፡ መሥዋዕት ሲሠዋበትና ሕዝቡ አምልኳቸውን ሲፈጽሙበት የኖሩት የብሉይ ኪዳኑ ቤተ መቅደስ የታነጸበት ቦታ የተሠራው እነዚህ ሁለቱ ወንድማማቾች የተገናኙበት ቦታ ላይ ነው ይላሉ፡፡ እኛ እንዲህ ብንተሳሰብ እግዚአብሔር እርሱ የሚመሰገንበትን እኛም በፍቅር አንድ የምንሆንበትን መንፈስ ይሰጠናል፡፡

 

ለራሳችንና የእኛ ወገን ለምንለው ብቻ እንድንጠቀም፣ የእኛ ወገን ወይም ቡድን ወይም አካባቢ ብቻ ቀዳሚ ወይም የተለየ ተጠቃሚ እንዲሆን በማስላት የምንሠራው ሥራ ግን ራሳችንንም አይጠቅምም፡፡ ስለሆነም እንኳን በክርስትና ሃይማኖት እኖራለሁ ለሚል ሰው ቀርቶ በፖለቲካ እንኳ እየተጠላ ያለውን እንዲህ ዓይነት አስተሳሰብ እግዚአብሔር ከውስጣችን እንዲያወጣልንና ነጻ እንዲያደርገን እንለምነው፡፡ ለሁላችንም የሚጠቅመወን ለቤተ ክርስቲያን የሚበጀውን በአንድ ልብ ለማሰብ እንሞክር፡፡

4. ወደ እግዚአብሔር እንጸልይ

ነቢዩ ዳዊት “ወከዐው ልበክሙ ቅድሜሁ – ልባችሁን (ሃሳባችሁን፣ ልመናችሁን) በፊቱ አፍሱ (ንገሩት፣ ግለጡለት)” እንዳለ ጸሎት ጭንቀታችንንና ሃሳባችንን ለአባታችን ለእግዚአብሔር የምንገልጥበት ልዩ ሀብት ነው፡፡ ከእኛ በላይ ለእኛ የሚያስፈልገንን የሚያውቅ፣ ከአባታዊ ቸርነቱ የተነሣ የሚጠቅመንን እንጂ የሚጎዳንን የማይሰጥ እርሱን በጸሎት እንጠይቀው፡፡ ድካማችንን የሚያውቅ እርሱ በጸሎት ወደ እርሱ እንደንጠይቀው በቅዱሳት መጻሕፍት በተለያየ መንገድ ደግሞ ደጋግሞ አስተምሮናል፡፡ “ለምኑ፣ ይሰጣችሁማል፤ ፈልጉ፣ ታግኙማላችሁ፤ መዝጊያን አንኳኩ፣ ይከፈትላችሁማል፡፡ የሚለምን ሁሉ ይቀበላልና፣ የሚፈልግም ያገኛል” በማለት ደጋግሞ ካስተማረ በኋላ በምሳሌ ደግሞ እንዲህ አለ፡- “አባት ከሆናችሁ ከእናንተ ከማናችሁም ልጁ እንጀራ ቢለምነው እርሱም ድንጋይ ይሰጠዋልን? ዓሣ ደግሞ ቢለምነው በዓሣ ፋንታ እባብ ይሰጠዋልን? ወይስ እንቁላል ቢለምነው ጊንጥ ይሰጠዋልን? እንኪያስ እናንተ ክፉዎች ስትሆኑ ለልጆቻችሁ መልካም ስጦታ መስጠት ካወቃችሁ በሰማይ ያለው ያለው አባት ለሚለምኑት እንዴት አብልጦ መንፈስ ቅዱስን ይሰጣቸው?” ሉቃ. 11፡9-13

 

ስለዚህ ብንለምነው የማይሰለቸን፣ ይልቁንም ሳንለምነው ከምንቀር ብንለምነው የሚወድ ቸር አባት እግዚአብሔር እያለን እንዴት የምንሻውን እናጣለን? ሆኖም ስንለምነው ፈቃዱን አውቀን በቅዱሳት መጻሕፍት በታዘዝነው መሠረት ይሆን ዘንድ፣ እንደ ታዘዝነው ለመሆን እንድንችልም ራሳችንን በሚቻለን እያዘጋጀን ሊሆን ይገባል፡፡ እንዲህ ከሆነ ሁሉንም በእኩል ዓይን የሚያይ፣ የወንጌል የመዳን ጸጋ ለሰው ሁሉ እንዲደርስ የሚተጋ፣ በጎቹን በትጋት የሚጠብቅና ስለ አንዲቷ በግ መባዘን ዕረፍት የሚያጣ ደግ እረኛ ይሰጠን ዘንድ ይችላል፡፡

 

እግዚአብሔር አምላክ “አንብር ለነ ኖላዌ ኄረ ዲበ መንበሩ – በመንበሩ ላይ ቸር እረኛ አስቀምጥልን (አምጣልን)” ብለን የምንጸልየውን ጸሎት ተቀብሎ ቅን መሪ ይስጠን፡፡ አሜን፡፡

የጥናትና ምርምር ማእከል 4ኛ ዓመታዊ የጥናት ጉባኤ ሊካሄድ ነው፡፡

ነሐሴ 18 ቀን 2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ


“በማኅበረ ቅዱሳን የጥናትና ምርምር ማእከል   ለነሐሴ 19 እና 20 ሊያካሂደው የነበረው የጥናት ጉባኤ በቤተ ክርስቲያናችን በተከሰተው የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ ዜና እረፍት ምክንያት ጉባኤውን ማካሄድ ባለመቻላችን ይቅርታ እየጠየቅን መርሐ ግብሩ ወደ ጳጉሜ 3 እና 4 ቀን 2004 ዓ.ም. መተላለፉን እንገልጻለን” በማለት ምክትል ዳይሬክተር አቶ ሰይፈ አበበ ገለጹ፡፡

 

በጥናቱ ላይ ከተካተቱት ዋና ዋና ርዕሰ ጉዳዮች መካከል የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ቅርሶች ጥበቃና አያያዝ፣ የሕግ አገልግሎት በቤተ ክርስቲያን፣ የአብነት ትምህርት ቤቶች ለሀገር ያበረከቱት አስተዋጽኦ፣ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ካህናት አባቶች ሚና  በምክክር አገልግሎት፣ The role of folklore in controlling sexual behavior in Christian context, አንዳንድ ነጥቦች ስለማኅበረ ቅዱሳን፣ ኅትመቶች አስተዳደራዊና ሀገር አቀፋዊ ጉዳዮች አዘጋገብ የተሰኙት ይገኙበታል፡፡

 

በእያንዳንዱ ርዕሰ ጉዳይ ላይ ጥናቱን የሚያቀርቡት የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ምሁራን ሲሆኑ ሰፊ ውይይት እንደሚካሄድባቸው የጥናትና ምርምር ማእከሉ ምክትል ዳይሬክተር  ገልጸዋል፡፡

abune paulos funeral1

የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ሥርዓተ ቀብር ተፈጸመ

“ከመቃብር ላይ ሆነን የምንናገረው ስለ ትንሣኤ እሙታን ነው” ብፁዕ አቡነ ናትናኤል ዐቃቢ መንበረ ፓትርያርክ

ነሐሴ 17 ቀን 2004 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኩኖ አምላክ

abune paulos funeral1 ብፁዕ ወቅዱስ ዶክተር አቡነ ጳውሎስ ቀዳማዊ፣ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ፣ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት፣ የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ፕሬዝደንት፣ የዓለም ሃይማኖቶች ለሰላም የክብር ፕሬዝዳንት ሥርዓተ ቀብራቸው ዛሬ ነሐሴ 17 ቀን 2004 ዓ.ም እኩለ ቀን ላይ በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ቤተክርስቲያን ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት፣ ከአኀት አብያተ ክርስቲያናትና ከሌሎችም የተወከሉ የእምነት አባቶች በሺዎች የሚቆጠሩ ምእመናን በተገኙበት ተፈጽሟል፡፡

Abune Paulos FuneralAbune Paulos Funeral0Abune Paulos Funeral

Abune Paulos Funeral15

Abune Paulos Funeral2Abune Paulos Funeral4 Abune Paulos Funeral9

Abune Paulos Funeral5Abune Paulos Funeral00Abune Paulos Funeral6

Abune Paulos Funeral10Abune Paulos Funeral11Abune Paulos Funeral13Abune Paulos Funeral14

Abune Paulos Funeral7Abune Paulos Funeral8

የቅዱስነታቸው አስክሬን ትናንት ረቡዕ (ነሐሴ 16 ቀን 2004ዓ.ም) ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ በካህናት ፣በሰንበት ትምህርት ቤቶች ዘማሪያንና በምእመናን ታጅቦ ከመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም ወደ መንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ከተወሰደ በኋላ በዚሁ ቤተ ክርስቲያን ጸሎተ ፍትሐትና ማኅሌት ሲደርስ አድሯል፡፡ ዛሬ ንጋት ላይ ጸሎተ ቅዳሴው ከተከናወነ በኋላ ከግብፅ፣ከሶርያ፣ ከሕንድና ከአርመን ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አኀት አብያተ ክርስቲያናት የተወከሉ አባቶች በየቋንቋቸው ጸሎት አድርሰዋል፡፡

በሥርዓተ ቀብሩ ላይ የኢ.ፌ.ድ.ሪ ፕሬዝደንት  የተከበሩ አቶ ግርማ ወልደ ጊዮርጊስ የላኩትን የሐዘን መግለጫ በተወካያቸው አቶAbune Paulos Funeral14 አሰፋ ከሲቶ አማካኝነት የቀረበ ሲሆን፣ በተመሳሳይ የኢ.ፌ.ድ.ሪ ጊዚያዊ ጠቅላይ ሚንስትርና የውጭ ጉዳይ ሚንስትር  አቶ ሃይለ ማርያም ደሳለኝ፣ እንዲሁም የአዲስ አባባ ከንቲባ ኩማ ደመቅሳ በየተራ በቅዱስነታቸው ዕረፍት ምክንያት የተሰማቸውን ልባዊ ሐዘን ገልጠዋል፡፡

Abune Paulos Funeral Liturgyሥርዓተ ቀብሩን በመምራት ያስፈጸሙት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አቃቤ መንበርና የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ናትናኤል ባስተላለፉት ቃለ ምእዳንና ጸሎተ ቡራኬ፡-“…እኛ ከዚህ መቃብር ላይ ሆነን የምንናገረው ስለ መቃብር አይደለም፤ ስለ ትንሣኤ ሙታን ነው እንጂ፤ ” ብለዋል፡፡ ብፁዕነታቸው በዚሁ መልእክታቸው የቅዱስ ፓትርያርኩን ቅድስና አውስተው ለመላው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናንና ምእመናት መጽናናትን ተመኝተዋል፡፡ የሕይወት ታሪካቸውን ይህን በመጫን ያንብቡ

abune paulos

ነሐሴ 17/2004 ዓ.ም. ቀጥታ ስርጫት ከመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ

abune paulos

 

ቀጣይ ያለውን መርሀ ግብር ለማቅረብ ከቦታ ጥበትና ከሰው መጨናነቅ የተነሣ ማስተላለፍ ስላልቻልን ከቀብር ስነ ሥርዓቱ በኋላ የመርሀ ግብሩን ሁኔታ በዝርዝርና በፎቶ ግራፍ የምናቀርብ ይሆናል፡

6:00 የኢትዮጵያ ሀይማኖቶች አንድነትን ጉባኤ በመወከል ሼህ አህመዲን የሀዘን መግለጫ እያስተላለፉ ነው፡፡
5:49 የኖርዌይ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ የሀዘን መግለጫ መልዕክት እያስተላለፉ ነው፡፡

5፡44 የሮማ ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ፖፕ የሀዘን መግለጫ  መልዕክት በተወካያቸው  እየቀረበ ነው፡

5:38 የሶርያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ተወካይ የሀዘን መግለጫ እያቀረቡ ናቸው፡

5፡32 የምሥራቅ አብያተ ክርስቲያናት ተወካይ መልዕክት እያስተላለፉ ነው፡

ከኢፌዲሪ ም/ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ክቡር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ  መልዕክት በንግግራቸው ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ፡-
•    ቤተ ክርስቲያኗን በዓለም መድረክ እንዳስተዋወቁ ፣
•    በሀገሪቷ የተከሰተውን የኤች. አይ.ቪ ኤድስ በሽታን እንደተከላከሉ
•    በሀገራችን ባሉ ሀይማኖቶች መካከል ሰላምና መግባባት እንዲኖር እንደሰሩ፣
•    የሰላም አምባሳደር በመሆን ከኢትዮጵያ አልፈው በዓለም መድረክ ከፍተኛ ሚና እንደተጫወቱ ገልጸዋል፡፡
•    ተተኪ የቤተ ክርስቲያኗ መሪዎችም የቅዱስነታቸውን አርአያ ተከትለው መልካም አስተዳደርን በቤተ ክርስቲኗ እንዲያሰፍኑ መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡

5፡26 የኮፕት ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን አቃቤ መንበር አቡነ ጳኩሚስ መልዕክት እያስተላለፉ ነው፡

5፡22 የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳደር ከንቲባ አቶ ኩማ ደመቅሳ የሀዘን መግለጫ መልዕክት እያስተላለፉ ነው፡

5፡14 የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ህብረት ፕሬዝዳንት ህብረቱን በመግለጽ የሀዘን መግለጫ እያስተላለፉ ነው፡፡5፡14 የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ህብረት ፕሬዝዳንት ህብረቱን በመግለጽ የሀዘን መግለጫ እያስተላለፉ ነው፡፡

5፡09 የኢፌዲሪ ፕሬዝዳንት መልዕክት በተወካዩ አቶ አሰፋ ቀሲቶ አማካኝነት በመነበብ ላይ ነው፡

5፡05 የኢፌዲሪ ም/ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ክቡር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ የሀዘን መግለጫ መልዕክት በማስተላለፍ ላይ ናቸው፡፡

4፡54 ከአዲስ አበባ ሰንበት ትምህርት ቤቶች የተውጣጡ የሰንበት ትምህርት ቤት መዘምራን ያሬዳዊ ዜማ እያቀረቡ ናቸው፡፡

4:30 ከአዲስ አበባ አድባራትና ገዳማት የተውጣጡ ካህናት ያሬዳዊ ዜማ እያቀረቡ ናቸው፡፡

4፡54 ከአዲስ አበባ ሰንበት ትምህርት ቤቶች የተውጣጡ የሰንበት ትምህርት ቤት መዘምራን ያሬዳዊ ዜማ እያቀረቡ ናቸው፡፡

4፡22 የግሪክ ኦርቶዶክስ ቤተ ክስቲያን ልዑካን ጸሎት በማድረግ ላይ ናቸው፡፡

በቅርቡ ከዚህ ዓለም በሞት በተለዩት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሲኖዳ የቀብር ሥነ ሥርዓት ላይ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ የተመራው የብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ልዑክ ጸሎት ማድረጉ ይታወሳል፡፡

በአንድ እኅት ቤተ ክርስቲያን የዚህ ዓይነት ሐዘን በሚደርስበት ጊዜ በሌሎች አኃት አብያተ ክርስቲያናት ተወካዮች ጸሎት መደረጉ የተለመደ ሥርዓት ነው፡፡

4:13 የሕንድ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ልዑካን ጸሎት በማድረግ ላይ ናቸው፡፡

4፡04 የአርመንያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ልዑካን ጸሎት በማድረግ ላይ ናቸው፡፡

3፡55 በኮፕት ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ዐቃቤ መንበር መሪነት ከቤተ ክርስቲያኗ የመጡ ካህናት ጸሎት እያደረጉ ነው፡፡

በዕለቱ እየጣለ ባለው ዝናብ የተነሣ መርሀ  ግብሩ እየተከናወነ ያለው በዐውደ ምሕረቱ ላይ በተጣሉ ድንኳኖች ሥር ነው፡፡

3፡35 መርሐ ግበሩ በጸሎተ ወንጌል እየተከፈተ ነው፡፡

3፡30 በዐውደ ምሕረቱ ክቡራን የመንግሥት ተወካዮች፣ ዲፕሎማቶች፣ የልዩ ልዩ አብያተ ክርስቲያናት መሪዎች፣ የአድባራትና ገዳማት አለቆች፣ ካህናት ፣ መዘምራንና ምዕመናን ታድመዋል፡፡

3፡20 ጸሎተ ቅዳሴውና ቀኖና የሚያዝዘው ጸሎት ሁሉ ተፈጸሞ በአሁኑ ሰዓት አስከሬኑ ወደ ዐውደ ምሕረቱ ወጥቷል፡፡

Normal 0 false false false EN-US X-NONE AR-SA

4:30 ከአዲስ አበባ አድባራትና ገዳማት የተውጣጡ ካህናት ያሬዳዊ ዜማ እያቀረቡ ናቸው፡፡

4፡54 ከአዲስ አበባ ሰንበት ትምህርት ቤቶች የተውጣጡ የሰንበት ትምህርት ቤት መዘምራን ያሬዳዊ ዜማ እያቀረቡ ናቸው፡፡

5፡05 የኢፌዲሪ ም/ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ክቡር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ የሀዘን መግለጫ መልዕክት በማስተላለፍ ላይ ናቸው፡፡

የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ቀብር ሥነ ሥርዓት መርሐ ግብር

“ለፈራሔ እግዚአብሔር ይሤኒ ደኅሪቱ፣ ወይትባረክ ዕለተ ሞቱ”

እግዚአብሔርን የሚፈራ ሰው ፍጻሜው ያምራል፡፡ በሚሞትበትም ቀን ይከበራል፡፡ ሲራ.1፥13፡፡

የብፁዕ ወቅዱስ ዶ/ር አቡነ ጳውሎስ ቀደማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቀነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ፕሬዝዳንት፣ የዓለም ሃይማኖቶች ለሰላም የክብር ፕሬዝዳንት፣ የዓለም የሰላም አምባሳደር የቀብር ሥነ ሥርዓት የወጣ መርሐ ግብር፡፡ ሙሉውን እዚህ በመጫን ያንብቡ

የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ የቀብር ሥነ ሥርዓት የቀጥታ ዘገባ

ነሐሴ 16 ቀን 2004 ዓ.ም.

{gallery count=1 width=350 height=300 counter=1 links=0 alignment=center animation=3000}kebre{/gallery}
  • 4፡00 የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ አስከሬን አርፎ ከሰነበተበት ከሐያት ሆስፒታል ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የደብር አስተዳዳሪዎች ካህናትና ቀሳውስት የሰንበት ትምህርት ቤቶች መዘምራን ዘመድ አዝማድና ምእመናን ታጅቦ ጠቅላይ ቤተ ክህነት  ስብከተ ወንጌል አዳራሽ ደረሰ፡፡

  • 4፡30 አስከሬኑ በመንበረ ፓትርያርክ ስብከተ ወንጌል አዳራሽ ካረፈ በኋላ መርሐ ግብሩ በብፁዕ አቡነ ናትናኤል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክና የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ጸሎት ተጀመረ፡፡

  • 4፡36 በርዕሰ አድባራት ወገዳማት አክሱም ጽዮን ካህናት ጸሎተ ወንጌል እየተደረሰ ነው፡፡

  • 4፡50 በብፁዕ አቡነ ናትናኤል መሪነት ጸሎተ ኪዳን እየተደረሰ ነው፡፡

  • 4፡57 በስብከተ ወንጌል አዳራሹ የነበረው መርሐ ግብር ተጠናቆ የቅዱስነታቸው አስከሬን ወደ መንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ቅድስት ማርያም ገዳም እየተወሰደ ነው፡፡

  • 8፡30 ጸሎተ ቅዳሴው ተጠናቋል፡፡ በተያዘው መርሐ ግብር መሠረት የቅዱስነታቸው አስከሬን በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የአድባራት አለቆች፣ የሰንበት ትምህርት ቤት መዘምራንና ምእመናን እንዲሁም ክቡራን እንግዶች ታጅቦ ወደ ወንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ጉዞ ጀምሯል፡፡

  • 9፡50 የቅዱስነታቸው አስከሬን በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የአድባራት አለቆች፣ የሰንበት ትምህርት ቤት መዘምራንና ምእመናን እንዲሁም ክቡራን እንግዶች ታጅቦ ወደ ወንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል  እያመራ ሲሆን አሁን አራት ኪሎ አደባባይ ደርሷል፡፡

  • 10፡25 የቅዱስነታቸው አስከሬን በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካትድራል በክብር ደርሷል፡፡