ቀዳም ሥዑር

ሚያዝያ 6፣2004 ዓ.ም.

ቅዳሜ፡

ቀዳም ሥዑር ይባላል፡፡ በዚች ዕለች ከድሮው በተለየ መልኩ የጌታችንን መከራ በማሰብ በጾም ታስባ ስለምትውል የተሻረችው ቅዳሜ ትባላለች፡፡

የማትጾመዋ ቅዳሜ ስለምትጾም ስዑር /የተሻረች/ ተብላለች በዓል መሻርን አይመለከትም በቀዳም ሥዑር  ሌሊት ሥርዓቱ የሚጀመረው በመኀልየ ሰሎሞን ምንባብ ነው፡፡ ማኀሌቱም እዝሉ እየተቃኘ እየተመጠነ፣ እየተዘመመ እየተመረገደ እየተጸፋ ያድራል፡፡ ጥዋት አቡን መዋሥዕት ውዳሴ ማርያም ዜማ ተደርሶ ወለመልአከ ሕይወትሰ ሰቀልዎ በሚለው ሰላም ይጠናቀቃል፡፡በዚህ ዕለት ልብሰ ተክህኖ የለበሱ ካህናትና ዲያቆናት ቄጤማ ተሸክመው ቃጭል ሲያቃጨሉ መታየታቸው ዕለተ ትንሣኤውን ለሚናፍቅ ምእመን ትልቅ ብስራት ነው፡፡

 

ለምለም ቅዳሜ፡- ካህናቱ ለምእመናን ለምለም ቀጤማ የሚያድሉበት ዕለት ስለሆነ በዚህ ተሰይሟል፡፡ ቀጤማውንም ምእመናን እስከ ትንሣኤ ሌሊት በራሳቸው ላይ ያስሩታል፡፡

በቀዳም ስዑር ቀሳውስቱና ዲያቆናቱ ቃጭል /ቃለዓዋዲ/ እየመቱ ገብረ ሰላመ በመስቀሉ ትንሣኤሁ አግሃደ የሚለውን ያሬዳዊ ዜማ በመዘመር፤ ጌታ በመስቀሉ ሰላምን እንደሰጠን እና ትንሣኤውንም እንደገለጠልን በማብሰር፤ ቄጤማውን ለምእመናን ይሰጣሉ፡፡ ምእመናኑም በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የሚውል ገጸ በረከት ያቀርባሉ፡፡ ቄጤማውንም በራሳቸው ያስራሉ፡፡ ይህም አይሁድ ጌታችንን እያሰቃዩ ሊሰቅሉት ባሉ ጊዜ የእሾህ አክሊል ጭንቅላቱ ላይ ያሠሩበትን ድርጊት የሚያስታውስ ነው፡፡  

የቀጤማው አመጣጥና ምስጢርም ከአባታችን ከኖኅ ታሪክ ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ምድር በማየ አይኅ /በጥፋት ውኃ/ በጠፋችበት ወቅት የኖኅ ታማኝ መልእክተኛ ርግብ የውኃውን መጉደል ያበሰረችው ቀጤማ ይዛ በመግባት ነው፡፡

ዛሬም ለሐዲስ ኪዳን ክርስቲያኖች የኃጢአት ውኃ ጐደለ፣ የኃጢአት ውኃ ጠፋ በክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ነጻነት ተሰበከ ታወጀ በማለት ካህናት ቄጠማ ይዘው ምእመናንን ያበሥሩበታል፡፡

ቅዱስ ቅዳሜ ይባላል፡፡ ቅዱስ ቅዳሜ መባሉ ቅዱስ የሆነ እግዚአብሔር በጥንተ ተፈጥሮ ፍጥረታትን አከናውኖ ከፈጠረ በኋላ በዚህ ቀን ከሥራው ሁሉ ያረፈበት ነው፡፡ በዘመነ ሐዲስ ደግሞ የማዳን ሥራውን ሁሉ ፈጽሞ በሥጋው በመቃብር ሲያርፍ፣ በነፍሱ ሲዖልን በርብሮ ባዶዋን አስቀርቷታል፡፡ በዚያ ለነበሩት ነፍሳትም የዘለዓለም ዕረፍትን ያወረሰበት ዕለት ስለሆነ ከሌሎቹ ዕለታት የተለየ ዕለት ለማለት ቅዱስ ቅዳሜ ተብሏል፡፡

ምእመናን ሆይ፣ በአጠቃላይ ሥርዓተ ሕማሙን፤ ሰሙነ ሕማማት ብለው የተለየ ሥርዓት አውጥተው አባቶቻችን ተግተው ያቆዩልንን ሥርዓተ መላእክት ልንጠብቀውም ልንጠቀምበት ይገባል፡፡ የዕለታቱን ክብርና ስያሜ ከማወቅና ከመረዳት ጋር በዕለታቱ የታዘዙትን ሃየማኖታዊ ግዴታዎችን መወጣት ከሁላችንም ይጠበቃል፡፡

ምንጭ፡- ስምዐ ተዋሕዶ የስምዐ ጽድቅ ልዩ እትም ዘሰሙነ ሕማማት፣ ማኅበረ ቅዱሳን፣ ሚያዝያ 2004፣ አዲስ አበባ፡፡

የትንሣኤ የቅዳሴ ምንባብ 4( ዮሐ.20፥1-19)

ከሳምንቱም በመጀመሪያዉ ቀን ማርያም መግደላዊት በማለዳ ገና ጨለማ ሳለ ወደ መቃብር መጣች፤ ድንጋዩንም ከመቃብሩ አፍ ተነሥቶ አገኘችው፡፡ ፈጥናም ወደ ስምዖን ጴጥሮስና ጌታችን ኢየሱስ ይወደው ወደ ነበረው ወደዚያ ወደ ሌላዉ ደቀ መዝሙር መጥታ፥ “ጌታዬን ከመቃብር ወስደውታል፤ ወዴትም እንደ ወሰዱት አላውቅም” አለቻቸው፡፡ ጴጥሮስና ያ ሌላዉ ደቀ መዝሙርም ወጥተው ወደ መቃብሩ ሄዱ፡፡ ሁለቱም በአንድነት ሲሮጡ ያ ሌላዉ ደቀ መዝሙር ጴጥሮስን ቀድሞት ወደ መቃብሩ ደረሰ፡፡ ጐንበስ ብሎም ሲመለከት በፍታዉን ተቀምጦ አየ፤ ነገር ግን ወደ ውስጥ አልገባም፡፡ ስምዖን ጴጥሮስም ተከትሎት ደረሰና ወደ መቃብሩ ገባ፤ በፍታዉንም በአንድ ወገን ተቀምጦ አየ፤ በራሱ ላይ የነበረው መጠምጠሚያም ሳይቃወስ ለብቻው ተጠቅልሎ አየ፤ ከበፍታዉ ጋርም አልነበረም፡፡ ከዚህም በኋላ አስቀድሞ ወደ መቃብሩ የደረሰው ሌላዉ ደቀ መዝሙር ገባ፤ አይቶም አመነ፤ ከሙታን ተለይቶ ይነሣ ዘንድ እንደ አለው በመጻሕፍት የተጻፈውን ገና አላወቁም ነበርና፡፡ ከዚህም በኋላ ደቀ መዛሙርቱ ተመልሰው ወደ ቤታቸው ገቡ፡፡
ማርያም ግን ከመቃብሩ በስተውጭ እያለቀሰች ቆማ ነበረ፤ እያለቀሰችም ወደ መቃብሩ ጐንበስ ብላ ተመለከተች፡፡ ሁለት መላእክትንም ነጭ ልብስ ለብሰው የጌታችን የኢየሱስ ሥጋ በነበረበት ቦታ አንዱ በራስጌ፥ አንዱም በግርጌ ተቀምጠው አየች፡፡ እነዚያ መላእክትም፥ “አንቺ ሴት፥ ምን ያስለቅስሻል?” አሉአት፤ እርስዋም፥ “ጌታዬን ከመቃብር ውስጥ ወስደውታል፤ ወዴትም እንደ ወሰዱት አላውቅም” አለቻቸው፡፡ ይህንም ተናግራ ወደ ኋላዋ መለስ ስትል ጌታችን ኢየሱስን ቆሞ አየችው፤ ጌታችን ኢየሱስም እንደ ሆነ አላወቀችም፡፡ ጌታችን ኢየሱስም፥ “አንቺ ሴት፥ ምን ያስለቅስሻል? ማንንስ  ትሺያለሽ?” አላት፤ እርስዋ ግን የአትክልት ቦታ ጠባቂ መስሎአት፥ “ጌታዬ፥ አንተ ወስደኸው እንደ ሆነ ሄጄ ወደ እኔ እንዳመጣውና ሽቱ እንድቀባው ወዴት እንደ አኖርኸው ንገረኝ” አለችው፡፡ ጌታችን ኢየሱስም፥ “ማርያም!” አላት፤ እርስዋም መለስ ብላ በዕብራይስጥ ቋንቋ፥ “ረቡኒ!” አለችው፤ ትርጓሜዉም “መምህር” ማለት ነው፡፡ ጌታችን ኢየሱስም፥ “አትንኪኝ፤ ገና ወደ አባቴ አላረግሁምና፤ ነገር ግን ወደ ወንድሞቼ ሂጂና፡- ወደ አባቴ፥ ወደ አባታችሁ ወደ አምላኬ፥ ወደ አምላካችሁ አርጋለሁ አለ ብለሽ ንገሪአቸው” አላት፡፡ ማርያም መግደላዊትም ሄደች፤ ጌታን እንደ አየች፥ ይህንም እንዳላት ለደቀ መዛሙርቱ ነገረቻቸው፡፡
ያም ከሳምንቱ የመጀመሪያው ቀን በመሸ ጊዜ ደቀ መዛሙርቱ አይሁድን ስለ ፈሩ ተሰብስበው የነበሩበት ቤት ደጁ ተቈልፎ ሳለ ጌታችን ኢየሱስ መጥቶ በመካከላቸው ቆመና፥ “ሰላም ለእናንተ ይሁን” አላቸው፡፡

የትንሣኤ የቅዳሴ ምንባብ 3( ሐዋ.2፥22-37)

“እናንተ የእስራኤል ሰዎች ሆይ፥ ይህን ነገር ስሙ፤ እንደምታውቁት በመካከላችሁ እግዚአብሔር በእጁ ባደረገው በከሃሊነቱ በተአምራቱና በድንቅ ሥራዎቹ እግዚአብሔር የገለጠላችሁን ሰው የናዝሬቱን ኢየሱስን ስሙ፡፡ እርሱንም በተወሰነው በእግዚአብሔር ምክርና በቀደመው ዕውቀቱ እናንተ አሳልፋችሁ በኃጥኣን እጅ ሰጣችሁት፤ ሰቅላችሁም ገደላችሁት፡፡ እግዚአብሔር ግን የሞትን ማሰሪያ ፈቶ ከሙታን ለይቶ አስነሣው፤ ሞት እርሱን ሊይዘው አይችልምና፡፡ ዳዊትም ስለ እርሱ እንዲህ አለ፡- እግዚአብሔርን ሁል ጊዜ በፊቴ አየዋለሁ፤ እንዳልታወክ በቀኜ ነውና፡፡ ስለዚህ ልቤን ደስ አለው፤ አንደበቴም ሐሤት አደረገ፤ ሥጋዬም ደግሞ በተስፋው አደረ፡፡ ነፍሴን በሲኦል አትተዋትምና፥ ጻድቅህንም ጥፋትን ያይ ዘንድ አትሰጠውምና፡፡ የሕይወትን መንገድ አሳየኸኝ፤ ከፊትህ ጋራ ደስታን አጠገብኸኝ፡፡
“እናንተ ወንድሞች ሆይ፥ ስለ አባቶች አለቃ ስለ ዳዊት ነገር እንደ ሞተ እንደ ተቀበረም፥ መቃብሩም እስከ ዛሬ ድረስ በእኛ ዘንድ እንደ አለ ገልጬ እንድነግራችሁ ትፈቅዱልኛላችሁን? ነቢይ ስለ ነበረ፥ ከአብራኩም የተገኘውን በዙፋኑ እንዲያነግሥለት እግዚአብሔር መሐላን እንደ ማለለት ስለ ዐወቀ፥ ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ እንደሚነሣ፥ ሥጋዉም በመቃብር እንደማይቀር፥ ጥፋትንም እንደማያይ አስቀድሞ ዐውቆ ተናገረ፡፡ እርሱን ኢየሱስን እግዚአብሔር አስነሣው፤ ለዚህም እንደማያይ አስቀድሞ ዐውቆ ተናገረ፡፡ እርሱን ኢየሱስን እግዚአብሔር አስነሣው፤ ለዚህም እኛ ሁላችን ምስክሮቹ ነን፡፡ አሁን ግን በእግዚአብሔር ቀኝ ከፍ ከፍ ብሎና የመንፈስ ቅዱስን ተስፋ ከአብ ገንዘብ አድርጎ ይህን ዛሬ የምታዩትንና የምትሰሙትን አፈሰሰው፡፡ ዳዊት ወደ ሰማይ አልወጣም፥ ነገር ግን እርሱ አለ፡- ጌታ ጌታዬን አለው፡- በቀኜ ተቀመጥ፡፡ ጠላቶችህን ከእግርህ ጫማ በታች እስክጥላቸው ድረስ፡፡ እንግዲህ የእስራኤል ወገኖች ሁሉ እናንተ የሰቀላችሁትን ኢየሱስን እግዚአብሔር ጌታም መሢሕም እንዳደረገው በርግጥ ይወቁ፡፡” ይህንም በሰሙ ጊዜ ልባቸው ተከፈተ፤ ጴጥሮስንና ወንድሞቹ ሐዋርያትንም፥ “ወንድሞቻችን ሆይ፥ ምን እናድርግ?” አሏቸው፡፡

የትንሣኤ የቅዳሴ ምንባብ 2( 1ጴጥ.1፥1-13)

ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ ከጴጥሮስ፥ በጳንጦስ፥ በገላትያና በቀጰዶቅያ፥ በእስያና በቢታንያ ሀገሮች ለተበተኑ ስደተኞች፥ እግዚአብሔር አስቀድሞ እንዳወቃቸው፥ በመንፈስ ቅዱስም እንደሚቀደሱ፥ ይታዘዙና በኢየሱስ ክርስቶስ ደም ይረጩ ዘንድ፥ ለተመረጡት፥ ጸጋና ሰላም ይብዛላችሁ፡፡
ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን በመነሣቱ፥ ለሕያው ተስፋ እንደ ምሕረቱ ብዛት ሁለተኛ የወለደን የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አባት እግዚአብሔር ይመስገን፡፡ የማያረጀውን፥ የማይለወጠውንና የማይጠፋውን፥ በሰማያት ለእኛና ለእናንተ ተጠብቆልን ያለውን ለመውረስ፥ በኋላ ዘመን በሃይማኖት ትገለጥ ዘንድ ለተዘጋጀችው ድኅነት በእግዚአብሔር ኀይል ለተጠበቃችሁት፥ እስከ ዘለዓለም ደስ ይላችኋል፤ ነገር ግን በሚመጣባችሁ ልዩ ልዩ መከራ አሁን ጥቂት ታዝናላችሁ፡፡ በእሳት ከአጠሩት ከጥሩ ወርቅ በሚመረጥ ሃይማኖታችሁ እንደምትቀበሉት መከራ መጠን ኢየሱስ ክርስቶስ በሚገለጥበት ጊዜ በክብር፥ በጌትነትና በምስጋና ትገኛላችሁ፡፡ እርሱም ሳታዩት የምትወዱት ነው፤ እስከ ዛሬም ድረስ አላያችሁትም፤ ነገር ግን ታምኑበታላችሁ፤ አሁንም ፍጻሜ በሌላትና በከበረች ደስታ ደስ ይላችኋል፡፡ በሃይማኖታችሁም ፍጹምነት የነፍሳችሁን ድኅነት ታገኛላችሁ፡፡
ለእናንተም ስለሚሰጠው ጸጋ ትንቢት የተናገሩ ነቢያት የመረመሩአትና የፈለጉአት መድኀኒት ናት፡፡ በእነርሱም የነበረ የክርስቶስ መንፈስ ስለ ክርስቶስ መከራ፥ ከእርሱም በኋላ ስለሚመጣው ክብር፥ አስቀድሞ እየመሰከረ በምን ወይም እንዴት ባለ ዘመን እንዳመለከተ ይመረምሩ ነበር፡፡ ለእነርሱም ከሰማይ በተላከ በመንፈስ ቅዱስ ወንጌልን የሰበኩላችሁ ሰዎች አሁን በነገሩአችሁ ነገር እናንተን እንጂ ራሳቸውን እንዳላገለገሉ ተገለጠላቸው፡፡ ይህንም ነገር መላእክቱ ሊመለከቱ ይመኛሉ፡፡ ስለዚህ የልቡናችሁን ወገብ ታጥቃችሁና ነቅታችሁ ኑሩ፤ ኢየሱስ ክርስቶስም ሲገለጥ የምታገኙትን ጸጋ ፈጽማችሁ ተስፋ አድርጉ፡፡

የትንሣኤ የቅዳሴ ምንባብ 1 (1ቆሮ. 15፥20-41)

አሁንም ክርስቶስ ከሞቱ ሰዎች ሁሉ አስቀድሞ ተነሥቶአል፡፡ በመጀመሪያው ሰው ሞት መጥቶአልና፥ በሁለተኛው ሰው ትንሳኤ ሙታን ሆነ፡፡ ሁሉ በአዳም እንደሚሞት እንዲሁ በክርስቶስ ሁሉ ሕያዋን ይሆናሉ፡፡ ነገር ግን ሰው ሁሉ በየሥርዐቱ ይነሣል፤ በመጀመሪያ ከሙታን የተነሣ ክርስቶስ ነው፤ ከዚያ በኋላ በክርስቶስ ያመኑ እርሱ በሚመጣበት ጊዜ ይነሣሉ፡፡ እግዚአብሔር አብ መንግሥቱን እጅ ባደረገ ጊዜ፥ ገዥም ሁሉ፥ ንጉሥም ሁሉ፥ ኀይልም ሁሉ በተሻረ ጊዜ፥ያን ጊዜ ፍጻሜ ይሆናል፡፡ ጠላቶቹ ሁሉ ከእግሩ በታች እስኪወድቁ ድረስ ይነግሥ ዘንድ አለውና፡፡ ከዚያ በኋላ የመጨረሻው ጠላት ይሻራል፤ ይኸውም ሞት ነው፡፡ ሁሉን ከእግሩ በታች አስገዝቶለታልና፥ “ሁሉ ይገዛለት” ባለ ጊዜ ግን ሁሉን ከሚያስገዛለት በቀር እንደ ሆነ የታወቀ ነው፡፡ ሁሉም በተገዛለት ጊዜ ግን እግዚአብሔር በሁሉ ቦታ በሁሉ ይሆን ዘንድ፥ ያን ዕለት ወልድም ሁሉን ላስገዛለት ይገዛል፡፡
ያለዚያማ ለምን ያጠምቃሉ? ሙታን እንዲነሡ አይደለምን? እንግዲህ እኛስ ሁልጊዜ መከራን ስለምን እንቀበላለን? ወንድሞቻችን ሆይ፥ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ በሆነውና በእናንተ ላይ ባለኝ ትምክህት ሁል ጊዜ እገደላለሁ፡፡ በውኑ በኤፌሶን ከአውሬ ጋር የታገልሁ ለሰው ብዬ ነውን? ምንስ ይጠቅመኛል? ሙታን የማይነሡ ከሆነ እንግዲህ እንብላ እንጠጣ፥ ነገም እንሞታለን፡፡ ወንድሞቻችን አያስቱአችሁ፤ ክፉ ነገር መልካም ጠባይን ያበላሻልና፡፡
ለጽድቅ ትጉ፤ አትሳቱ፤ እግዚአብሔርን የማያውቁት ሰዎች አሉና፤ ነገር ግን እንድታፍሩ ይህን እላችኋለሁ፤ ሙታን እንዴት ይነሣሉ? የሚነሡስ በምን አካላቸው ነው? የሚል አለ፡፡ አንተ ሰነፍ! አንተ የምትዘራው እንኳን ካልፈረሰ አይበቅልም፡፡ የምትዘራውም የስንዴ ቢሆን፥ የሌላም ቢሆን የምትዘራት ቅንጣት ብቻ ናት እንጂ ይህ ኋላ የሚገኘው አገዳው አይደለም፡፡ እግዚአብሔር ግን እንደ ወደደ አገዳን ይሰጠዋል፤ ለእያንዳንዱ ዘርም አገዳው እየራሱ ነው፡፡ የፍጥረቱ ሁሉ አካል አንድ አይደለምና፤ የሰው አካል ሌላ ነው፤ የእንስሳም አካል ሌላ ነው፤ የወፍ አካልም ሌላ ነው፤ የዓሣ አካልም ሌላ ነው፡፡ ሰማያዊ አካል አለ፤ ምድራዊ አካልም አለ፤ ነገር ግን በሰማይ ያለው አካል ክብሩ ልዩ ነው፤ በምድርም ያለው አካል ክብሩ ልዩ ነው፤ የፀሐይ ክብሩ ሌላ ነው፤ የጨረቃም ክብሩ ሌላ ነው፤ የከዋክብትም ክብራቸው ሌላ ነው፤ ኮከብ ከኮከብ በክብር ይበልጣልና፡፡

የትንሣኤ የማሕሌት ምንባብ 3 (ሉቃ.24፥1-13)

ከሳምንቱም በመጀመሪያዪቱ ቀን ያዘጋጁትን ሽቶ ይዘው እጅግ ማልደው ወደ መቃብሩ ሄዱ፤ ሌሎች ሴቶችም አብረዋቸው ነበሩ፡፡ ያቺንም ድንጋይ ከመቃብሩ ላይ ተንከባልላ አገኙአት፡፡ ገብተውም የጌታችን የኢየሱስን ሥጋ አላገኙም ስለዚህም ነገር የሚሉትን አጥተው ሲያደንቁ ሁለት ሰዎች ከፊታቸው ቆመው ታዩአቸው፤ ልብሳቸውም ያብረቀርቅ ነበር፡፡ ፈርተውም ፊታቸውን ወደ ምድር አቀረቀሩ፡፡ እነርሱም እንዲህ አሉአቸው፥ “ሕያዉን ከሙታን ጋር ለምን ትሹታላችሁ? በዚህ የለም፤ ተነሥቶአል፡፡ በገሊላ ሳለ ለእናንተ እንዲህ ሲል የተናገረውን ዐስቡ፡- የሰው ልጅ በኀጢአተኞች ሰዎች እጅ ተላልፎ ይሰጥ ዘንድ አለው፤ ይሰቅሉታል፤ ይገድሉታል፤ በሦስተኛውም ቀን ይነሣል፡፡” ቃሉንም ዐስቡ፡፡ ከመቃብርም ተመልሰው ለዐሥራ አንዱና ለቀሩት ባልጀሮቻቸውም ይህን ለሐዋርያት ነገሩአቸው፡፡ ይህም ነገር በፊታቸው እንደ ተረት መሰላቸውና አላመኑአቸውም፡፡ ጴጥሮስም ተነሣ፤ ወደ መቃብርም ፈጥኖ ሄደ፤ ዝቅ ብሎም በተመለከተ ጊዜ በፍታውን ለብቻው ተቀምጦ አየ፤ የሆነውንም እያደነቀ ተመለሰ፡፡
በዚያም ቀን ከመካከላቸው ሁለት ሰዎች ከኢየሩሳሌም ስድሳ ምዕራፍ ያህል ወደምትርቀው ኤማሁስ ወደምትባለው መንደር ሄዱ፡፡

ትንሣኤ /ለሕፃናት/

ሚያዝያ 6/2004 ዓ.ም.

በልያ አበበ

ልጆች መግደላዊት ማርያምን ታውቋታላችሁ? መግደላዊት ማርያም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከፈወሳቸው ሕመምተኛ የነበሩ ሰዎች አንዷ ናት፡፡ ከነበረባት በሽታ ከዳነች ጊዜ ጀምሮ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሚያስተምረውን ትምህርት በሙሉ የምትከታተል እና እርሱንም የምታገለግል ነበረች፡፡
መግደላዊት ማርያም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአይሁድ እጅ ተገርፎ ሲሰቀል ከሌሎች ከገሊላ ከመጡ ብዙ ሴቶች ጋር ሆና በጣም አዝና በሩቅ ስትመለከት ነበር፡፡
ዮሴፍና ኒቆዲሞስ የተባሉት እግዚአብሔር የባረካቸው ደጋግ ሰዎች የጌታችንን ቅዱስ ሥጋ ከጲላጦስ ተቀብለው እያመሰገኑ በንጹሕ በፍታ ወይም የመግነዝ ጨርቅ ሲከፍኑት፤ በአዲስ መቃብርም አኑረው የመቃብሩን ደጃፍ ሲዘጉ መግደላዊት ማርያም በመቃብሩ አንጻር ተቀምጣ ትመለከት ነበር፡፡
አይሁድ የጌታችን መቃብርን እንዲጠብቁ ጠባቂ ወታደሮችን አዝዘው ነበር፡፡ መግደላዊት ማርያም እሑድ ዕለት በጠዋት የጌታችንን ቅዱስ ሥጋ ለመቀባት ያዘጋጀችውን ሽቱ ይዛ ሌሎቹንም ሴቶች አስከትላ ወደ መቃብሩ ወጣች፡፡ ወደመቃብሩ ስትደርስ የመቃብሩ ድንጋይ ተንከባሎ ነበር፡፡ በድንጋጤ ወደ ውስጥ ስትገባም የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ሥጋ አላገኘችውም፡፡ የጌታችንን ሥጋ ማን እንደወሰደው ልታውቅ አልቻለችም፡፡
እየሮጠችም ወደ ሐዋርያት መጥታ “ጌታን ከመቃብር ወስደውታል ወዴትም እንዳኖሩት አናውቅም” አለቻቸው፡፡ ጴጥሮስና ዮሐንስ ይህን በሰሙ ጊዜ ወጥተው ወደ መቃብሩ ሮጡ፡፡ ወደ መቃብሩ ውስጥ ሲመለከቱም የተከፈነበትን ጨርቅ ብቻ ተመለከቱ፡፡ ስለዚህም ወደ ቤታቸው ተመለሱ፡፡ መግደላዊት ማርያም ግን እያለቀሰች ከመቃብሩ ውጭ ቆማ ቆየች፡፡ ድንገት ወደ መቃብሩ ዝቅ ብላ ብትመለከት ሁለት መላእክት የጌታችን ሥጋ በነበረበት ቦታ ላይ ተቀምጠው አየች፡፡
እነርሱም ለምን እንደምታለቅስ ጠየቋት፡፡ እርስዋም “ጌታዬን ወስደውታል ወዴትም እንዳኖሩት አላውቅም” አለቻቸው፡፡ ይህንንም ብላ ወደ ኋላ ዘወር ስትል አንድ ሰው ቆሞ አየች፡፡ የአትክልት ቦታው ጠባቂ መስሏት፡፡ ሰውየው “ለምን ታለቅሻለሽ? ማንንስ ትፈልጊያለሽ?” አላት እርሷም የጌታዬን ሥጋ አንተ ወስደኸው ከሆነ ወዴት እንዳኖርኸው ንገረኝ” አለችው፡፡
ልጆች ያነጋግራት የነበረው ሰው ግን የአትክልት ቦታ ጠባቂው አልነበረም፡፡ ማን እንደሆነ አወቃችሁ? አዎ፡፡ የሚወደን ስለ እኛ የሞተልን ከሙታንም መካከል ተለይቶ በሦስተኛው ቀን የተነሣው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነበር፡፡ በመጨረሻም በስሟ ማርያም ብሎ ሲጠራት አወቀችው፡፡ ከሙታን ተለይቶ እንደተነሣ ለሐዋርያት በሙሉ እንድትነግር ላካት፡፡ እርሷም በደስታ ወደ ሐዋርያት ተመልሳ ነገረቻቸው፡፡ ልጆች ጌታችን ከሙታን ከተነሣ በኋላ በመጀመሪያ ያየችው መግደላዊት ማርያም ነበረች፡፡
ልጆች በጌታችን ትንሣኤ ደስ አልተሰኛችሁም? ክርስቲያኖች በሙሉ በትንሣኤ በዓል በደስታ እንዘምራለን አምላካችንን እናመሰግናለን፡፡ መልካም የትንሣኤ በዓል ይሁንላችሁ፡፡
ልጆች ይህን ታሪክ የምታገኙት ከመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ 20 ቁጥር 1 ላይ ነው፡፡

የትንሣኤ የማሕሌት ምንባብ 2 (ማር.16፥1-ፍጻሜ )

ሰንበትም ባለፈች ጊዜ ማርያም መግደላዊት፥ የያዕቆብ እናት ማርያም፥ ሰሎሜም መጥተው ሥጋዉን ሊቀቡ ሽቱ ገዙ፡፡ በእሑድ ሰንበትም እጅግ ማልደው ፀሐይ በወጣ ጊዜ፥ ወደ መቃብር ሄዱ፡፡ እርስ በርሳቸውም፥ “ድንጋዪቱን ከመቃብሩ አፍ ላይ ማን ያነሣልናል?” አሉ፤ ድንጋዪቱ እጅግ ታላቅ ነበረችና፡፡ አሻቅበውም በተመለከቱ ጊዜ ደንጋዪቱ ተንከባልላ አዩ፡፡ ወደ መቃብሩም በገቡ ጊዜ አንድ ጎልማሳ ነጭ ልብስ ለብሶ በስተቀኝ ተቀምጦ አገኙና ደነገጡ፡፡ እርሱም እንዲህ አላቸው፥ “አትደንግጡ፤ የተሰቀለውን የናዝሬቱን ኢየሱስን ትሻላችሁን? ተነሥቶአል፤ በዚህስ የለም፤ የተቀበረበትም ቦታ እነሆ፡፡ ነገር ግን፥ ሂዱና ለደቀ መዛሙርቱና ለጴጥሮስም ወደ ገሊላ እንደሚቀድማቸው ንገሩቸው፤ እንደ ነገራቸውም በዚያ ያዩታል፡፡” ከመቃብርም ወጥተው ሸሹ፤ ፍርሀትና ድንጋጤ ይዞአቸዋልና፤ ስለፈሩም ለማንም አልተናገሩም፤ ያዘዛቸውንም ሁሉ ለጴጥሮስና ለወንድሞቹ ተናገሩ፡፡ ጌታችን ኢየሱስም ከሙታን ተለይቶ ከተነሣ በኋላ ተገለጠላቸውና፥ ለዘለዓለም ሕይወት የሚሆን የማይለወጥ ቅዱስ ወንጌልን ለፍጥረቱ ሁሉ ከምሥራቅ እስከ ምዕራብ ይሰብኩ ዘንድ ላካቸው፡፡
በእሑድ ሰንበትም ማለዳ ተነሥቶ ሰባት አጋንንትን ላወጣላት ለማርያም መግደላዊት አስቀድሞ ታያት፡፡
እርስዋም ሄዳ ከእርሱ ጋር ለነበሩት ሲያዝኑና ሲያለቅሱ ሳሉ ነገረቻቸው፡፡ እነርሱ ግን ሕያው እንደ ሆነ፥ ለእርስዋም እንደ ተገለጠላት በሰሙ ጊዜ አላመንዋትም፡፡ ከዚህም በኋላ፥ ከእነርሱ ለሁለቱ ወደ ገጠር ሲሄዱ በሌላ መልክ ተገለጠላቸው፡፡ እነርሱም ደግሞ ሄደው ለባልንጀሮቻቸው ነገሩ፤ እነርሱንም ቢሆን አላመኑአቸውም፡፡ ከዚህም በኋላ፥ ደግሞ ዐሥራ አንዱ በማዕድ ተቀምጠው ሳለ ተገለጠላቸው፤ እንደ ተነሣ ያዩትን አላመኑአቸውምና ስለ ሃይማኖታቸው ጒድለት ገሠጻቸው፤ የልባቸውንም ጽናት ነቀፈ፡፡ እንዲህም አላቸው፥ “ወደ ዓለም ሁሉ ሂዱ፤ ለፍጥረትም ሁሉ ወንጌልን ሰበኩ፡፡ ያመነ የተጠመቀም ይድናል፤ ያላመነ ግን ይፈረድበታል፡፡ ይህችም ምልክት በስሜ የሚያምኑትን ትከተላቸዋለች፤ በስሜ አጋንንትን ያወጣሉ፤ በአዲስ ቋንቋም ይናገራሉ፡፡ እባቦችንም በእጃቸው ይይዛሉ፤ የሚጐዳቸውም ነገር የለም፤ የሚገድል መርዝ ቢጠጡም የሚጐዳቸው የለም፤ በድውያን ላይም እጃቸውን ይጭናሉ፤ ድውያኑም ይፈወሳሉ፡፡”
ጌታችን ኢየሱስም ከተነጋገራቸው በኋላ ወደ ሰማይ ዐረገ፤ በአባቱም በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀመጠ፡፡ እነርሱም ወጥተው ጌታ እየረዳቸው፥ ቃሉንም በማያቋርጥ ተአምር እያጸናላቸው በስፍራው ሁሉ አስተማሩ፡፡
ከሰባ ሁለቱ አርድእት አንዲ ወንጌላዊው ማርቆስ የጻፈው ወንጌል ተፈጸመ፤ የጻፈውም በሮም ሀገር በሮማይስጥ ቋንቋ፤ ጌታችን በሥጋ ወደ ሰማይ ባረገ በዐሥራ አንድ ዓመት፥ ቀላውዴዎስ ቄሣር በነገሠ በአራት ዓመት ነው፡፡
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን፡፡ አሜን፡፡

የትንሣኤ የማሕሌት ምንባብ 1 (ማቴ.28፥1-ፍጻሜ )

በሰንበትም ማታ ለእሑድ አጥቢያ ማርያም መግደላዊትና ሁለተኛዋ ማርያም መቃብሩን ሊያዩ መጡ፡፡ እነሆ፥ ታላቅ የምድር መናወጥ ሆነ፤ የእግዚአብሔር መልአክ ከሰማይ ወርዶአልና፤ ቀርቦም በመቃብሩ አፍ ላይ ድንጋይዋን አንከባሎ በላይዋ ተቀመጠ፡፡ መልአኩም እንደ መብረቅ፥ ልብሱም እንደ በረዶ ነጭ ነበረ፡፡ እርሱንም ከመፍራት የተነሣ መቃብሩን የሚጠብቁ ታወኩ፤ እንደ በድንም ሆኑ፡፡ መልአኩም መልሶ ሴቶችን እንዲህ አላቸው፤ “እናንተስ አትፍሩ፤ የተሰቀለውን ኢየሱስን እንደምትሹ አውቃለሁና፡፡ በዚህ የለም፤ እርሱ እንደ ተናገረው ተነሥቶአል፤ ነገር ግን ኑና ተቀብሮበት የነበረውን ቦታ እዩ፡፡ ፈጥናችሁም ሂዱና፡- ከሙታን ተለይቶ ተነሣ፤ እነሆ፥ ወደ ገሊላ ይቀድማችኋል፤ በዚያም ታዩታላችሁ፤ ብላችሁ ለደቀ መዛሙርቱ ንገሩአቸው፤ እነሆም፥ ነገርኋችሁ፡፡” በፍርሀትና በታላቅ ደስታም ከመቃብሩ ፈጥነው ሔዱ፤ ለደቀ መዛሙርቱም ይነግሩአቸው ዘንድ ሮጡ፡፡ እነሆም፥ ጌታችን ኢየሱስ አገኛቸውና፥ “ሰላም ለእናንተ ይሁን” አላቸው፤ እነርሱም ቀርበው እግሩን ይዘው ሰገዱለት፡ ከዚህም በኋላ ጌታችን ኢየሱስ እንዲህ አላቸው፥ “አትፍሩ ሒዱና ወደ ገሊላ እንዲሄዱ ለወንድሞቼ ንገሩአቸው፤ በዚያም ያዩኛል፡፡”
እነርሱም ከሔዱ በኋላ ጠባቂዎች ወደ ከተማ ገብተው የሆነውን ሁሉ ለካህናት አለቆች ነገሩ፡፡ ተሰብስበውም ከሽማግሌዎች ጋር መክረው ለጭፍሮች ብዙ ገንዘብ ሰጡአቸው፡፡ እንዲህም አሏቸው፥ “ተኝተን ሳለን ደቀ መዛሙርቱ በሌሊት መጥተው ሰረቁት በሉ፡፡ ይህም ነገር በገዢው ዘንድ የተሰማ እንደ ሆነ እኛ እናሳምነዋለን፤ እናንተንም ያለ ሥጋት እንድትኖሩ እናደርጋለን፡፡” ጭፍሮችም ገንዘቡን ተቀብለው እንደ አስተማሩአቸው አደረጉ፤ ይህም ነገር እስከ ዛሬ ድረስ በአይሁድ ዘንድ ሲነገር ይኖራል፡፡
ዐሥራ አንዱ ደቀ መዛሙርት ግን ጌታችን ኢየሱስ ወደ አዘዛቸው ተራራ ወደ ገሊላ ሄዱ፡፡ ባዩትም ጊዜ ሰገዱለት፤ እኩሌቶቹ ግን ተጠራጠሩ፡፡ ጌታችን ኢየሱስም ቀርቦ እንዲህ ሲል ተናገራቸው፥ “ሥልጣን ሁሉ በሰማይና በምድር ተሰጠኝ፡፡ እንግዲህ ሂዱና በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው አሕዛብን ሁሉ አስተምሩ፡፡ ያዘዝኋችሁንም እንዲጠብቁ አስተምሩአቸው፤ እኔም እስከ ዓለም ፍጻሜ በዘመኑ ሁሉ ከእናንተ ጋር እኖራለሁ፡፡”
ከዐሥራ ሁለቱ ሐዋርያት አንዱ ሐዋርያ ማቴዎስ በምድረ ፍልስጥኤም በዕብራይስጥ ቋንቋ የጻፈው ወንጌል ተፈጸመ፤ መንፈስ ቅዱስ እያተጋው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሥጋ ወደ ሰማይ ካረገ በኋላ በስምንተኛው ዓመት፤ ቀላውዴዎስ ቄሣር በነገሠ በመጀመሪያዉ ዓመት ጻፈው፡፡
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን፡፡ አሜን፡፡
ejig yetekeberu_yealemloriet

እጅግ የተከበሩ የዓለም ሎሬት ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ አረፉ

ሚያዝያ 04፣ 2004ዓ.ም

እንዳል ደምስ

ejig yetekeberu_yealemlorietእጅግ የተከበሩ የዓለም ሎሬት ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ ባደረባቸው ሕመም ምክንያት በህክምና ሲረዱ ቆይተው በተወለዱ በ80 ዓመታቸው ሚያዚያ 2/2004 ዓ.ም. ምሽት ላይ ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል፡፡ እጅግ የተከበሩ የዓለም ሎሬት አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ ከአባታቸው ከአቶ ተክሌ ማሞ እና ከእናታቸው ከወ/ሮ ፈለቀች የማታወርቅ በጥቅምት ወር 1924 ዓ.ም. በአንኮበር ከተማ ተወልደዋል፡፡ የአንደኛ ደረጃ ትምህርታቸውን በአዲስ አበባ፣ እንዲሁም የከፍተኛ ትምህርታቸውን በእንግሊዝ አገር በሚገኘው የሥነ ጥበብ አካዳሚ በሥነ ስዕል በቅርፃ ቅርጽና በሥነ ሕንፃ ዲዛይን ተከታትለዋል፡፡

በነበራቸው የሥነ ስዕል ዝንባሌ ታላላቅ ሥራዎችን የሠሩ ሲሆን በወጣትነት ዘመናቸው በ1957 ዓ.ም. ከክቡር ዶክተር ከበደ ሚካኤል ጋር በኢትዮጵያው ንጉሠ ነገሥት ቀዳማዊ ኃ/ሥላሴ እጅ የመጀመሪያውን የኢትዮጵያ የሥነ ጥበብ ተሸላሚ ለመሆን ችለዋል፡፡ ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ የአራት ዓለም አቀፍ አካዳሚዎች አባል ሲሆኑ በተሰማሩበት የሥነ ሥዕል ጥበብ በዓለም ላይ ከፍተኛ ሚና ለተጫወቱ ታላላቅ ሰዎች የሚሰጠውን የዓለም ሎሬት የተሰኘውን ማዕረግ አግኝተዋል፡፡ እስካሁን ድረስም ከዘጠና ሰባት በላይ የዓለም አቀፍ ሽልማቶችን ከተለያዩ ተቋማት አግኝተዋል፡፡

ጊዜ የማይሽራቸው ታላላቅ የሥዕል ሥራዎች ለዓለም ያበረከቱ ሲሆን በስዕሎቻቸውም ሥርዓተ አምልኮን፣ ማኅበራዊ አኗኗር የማኅበረሰቡን ደስታና ሃዘንና ጀግንነቱን ሥልጣኔውና ሀገር ወዳድነትን የሚያንጸባርቁ ሥራዎችን አበርክተዋል፡፡ በተለይም ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ካላቸው ጥልቅ ፍቅርና እምነት በመነጨ ለተለያዩ ቤተ ክርስቲያናት እንዲሁም በስቱዲዮአቸውና በጸሎት ቤታቸው የሚገኙ መንፈሳዊ ስዕላትን አበርክተዋል፡፡ ከሠሯቸው መካከልም በገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን የሚገኙ በግድግዳ ላይ የተሠሩ መንፈሳዊ ስዕላትን በቀለም ቅብ፣ በባለቀለም ጠጠሮች፣ በክርክም መስታወቶችና በሞዛይክ ከታወቁትና ስመ ጥር ከሆኑት ሰዓሊ ብላታ እምአዕላፍ ኅሩይ ጋር ሠርተዋል፡፡ በተለያዩ ዓለም አቀፍ ሙዚየሞች ውስጥም ስዕሎታቸው በክብር ተቀምጠውላቸው በጎብኚዎች እየታዩ ይገኛሉ፡፡ ኢትዮጵያን በማስተዋወቅ ረገድም በስዕሎታቸውና በቅርፃቅርጾቻቸው አማካይነት ከፍተኛ ሚና የነበራቸው ሲሆን “ቪላ አልፋ” የተሰኘው ባለ 22 ክፍሎች መኖሪያ ቤታቸውና የግል ስቱዲዮአቸው ውስጥ ይህንኑ ለማንጸባረቅ ጥረት አድርገዋል፡፡

በቪላ አልፋ ስቱዲዮ ውስጥ የአክሱም ሐውልት፣ የጎንደር ፋሲለደስ፣ የሐረር ግንብ፣ የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት፣ ቅዱሳት ስዕላት፣ የተወለዱበት አንኮበር የሚገኘው ቤተ መንግሥት የሚያስደንቁ ባህላዊ፣ ታሪካዊ፣ ሃይማኖታዊና ሀገራዊ እሴቶችን አካቶ የያዘ ነው፡፡

በንግግራቸው ስመ እግዚአብሔርን መጥራት የሚያዘወትሩት እጅግ የተከበሩ የዓለም ሎሬት አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ በዋናው መግቢያ በራቸው ላይ “የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው” የሚል ጥቅስ በትልቁ ጽፈዋል፡፡ “እንደማንኛውም ዓይነት የጥበብ ሥራ በሠራሁ ጊዜ እኔ በጥበቤ ታላቅ ነኝ የሚል ትምክህት እንዳይቀርበኝ ዘወትር እንዳነበው ነው የጻፍሁት” በማለት ከዚህ በፊት በማኅበረ ቅዱሳን ለሚታተመው ሐመር መጽሔት ጋዜጠኞች መግለጻቸው ይታወሳል፡፡

በዓለማችን ላይ ከሚገኙ ስመጥርና ታላላቅ ከተሰኙ 200 ሰዎች ጋር የሕይወት ታሪካቸውንና የኢትዮጵያ ባንዲራ በጨረቃ ላይ እንዲያርፍ የተደረገ ሲሆን በደረሰባቸው የጨጓራ አልሰር ህመም ምክንያት በህክምና ሲረዱ ቆይተው በተወለዱ በ80 ዓመታቸው ማክሰኞ ምሽት ይህችን ዓለም ተሰናብተዋል፡፡ ሥርዓተ ቀብራቸው ሚያዚያ 6/2004 ዓ.ም. ቅዳሜ በቅድሥት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ይፈጸማል፡፡

ዝግጅት ክፍላችን ለመላው ቤተሰቦቻቸው ወዳጅ ዘመዶቻቸውና አድናቂዎቻቸው መጽናናትን ይመኛል፡፡