የማኅበረ ቅዱሳን 20ኛ ዓመት የምሥረታ በዓል በደማቅ መርሐ ግብር መከበር ይጀምራል፡፡

ሚያዚያ 20/2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደጀኔ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን ዓለም አቀፋዊ ማኅበራዊና መንፈሳዊ አገልግሎት የጀመረበትን 20ኛ ዓመት የምስረታ በዓሉን ማክበር ይጀምራል፡፡

የማኅበሩ የሕዝብ ግንኙነት ሓላፊ አቶ አክሊሉ ለገሠ እንደገለጹት ማኅበሩ 20ኛ ዓመት  የበዓል ዝግጅቱን ሚያዝያ 28 ቀን 2004 ዓ.ም. በጠቅላይ ቤተ ክህነት የሚያከብር ሲሆን በዓሉንም በሁሉም ማእከላትና ወረዳ ማእከላት በልዩ ልዩ መርሐ ግብራት ይካሄዳል፡፡

 

በዓሉን የተመለከተ ዘጋቢ ፊልም እና ትራክት የመጽሔተ ተልዕኮ ልዩ እትም መጽሔት መዘጋጅቱን የገለጹት ሓላፊው በዓሉ በአንድ ቀን የሚጠናቀቅ ሳይሆን በቀጣይ ተከታታይ መንፈሳዊ ዝግጅቶች እንደሚከበር ተናግረዋል፡፡

 

ማኅበረ ቅዱሳን “ለሁለንተናዊ የቤተ ክርስቲያን እድገት በጋራ እንሥራ” በሚል መሪ ቃል በሚያከበረው በዓል ቅዱስ ፓትርያርኩን ጨምሮ ሊቃነ ጳጳሳት፤ የጠቅላይ ቤተ ክህነት የመምሪያ ሓላፊዎች፣ የሰንበት ትምህርት ቤቶች ተወካዮች ማኅበራትና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች የሚገኙ መሆኑን ታውቋል፡፡

የአዳዲስ ፊዳላት፣ አዳዲስ ቁጥሮች፣ አፈጣጠር ሂደትና አስፈላጊነት

ሚያዚያ 20/2004 ዓ.ም.

ሠዓሊ አምሳሉ ገብረ ኪዳን አርጋው

ኢትዮጵያ ያሏትን መንፈሳዊና ቁሳዊ የታሪክ ዕሴቶች በማበርከት በኩል የቤተክርስቲያናችን ሊቃውንት ድርሻ ታላቅ መሆኑ ለማንም ግልጽ ነው፡፡ ከእነዚህ ዕሴቶቻችን መካከል ደግሞ በዓለም አቀፍ ደረጃ ስሟን የሚያስጠራና እንደ አፍሪካዊነታችን ብቸኛ ባለቤት እንድንሰኝ የሚያደርጉን ፊደላትና ቁጥሮች ናቸው፡፡ ይህን የሊቃውንቱን አርአያነት ያለው ተግባር ተከትለን የበለጠ ማርቀቅና ሃይማኖት ብቻ ሳይሆን በፍልስፍናና በፈጠራ ሥራውም ችግር ፈቺ በመሆን መራመድ እንዳለብን እናስባለን፡፡ ይህንን አስተሳሰብ ተከትሎ ወንድማችን አምሳሉ ‹‹የኢትዮጵያ ቁጥሮችና ፊደላት በየምክንያቱ ወደጎን እየተተዉ የእኛ ባልሆኑ እኛነታችንንም በሚያስረሱ ሌሎች ፊደላትና ቁጥሮች የመገልገል ዝንባሌ እየታዩ መምጣታቸው ያሳስበኛል በማለት አንድ አስተዋጽኦ ለሀገር ማበርከት አለብኝ ብሏል፡፡ እርሱ እንደሚለው የኢትዮጵያ ፊደላት እና ቁጥሮች በየትኛውም ቋንቋና አሠራር ውስጥ ውጤታማ ናቸው፡፡ አሉ የሚባሉ ውስንነቶችንም መቅረፍ የሚያስችል ዕምቅ አቅም አላቸው ይህንን አቅም እንዲኖራቸው አድርገው ሊቃውንቱ ቀምረው አልፈዋል፡፡ ስለዘህ ጥያቄ ሲነሣባቸው በፈጠራ አዳብረን ለትውልዱ እንዲመጥኑ አድርጎ አቅማቸውን መግለጽ ይቻላል ለዚህም የራሴን ጥረት አድርጌያለሁ፡፡ ስለዚህ የፈጠራ ረቂቄን አቅርቤ ሊቃውንትና የማኅበረ ቅዱሳን መካነ ድር አንባብያን የማኅበሩን መካነ ድርና የሐመር መጽሔትን ተጠቅመው እንዲተቹት፤ በዚህ ላይ ተመሥርቶም በዚሁ ረገድ የቤተክርስቲያን ሊቃውንትና የትውልዱ መነሣሣት እንዲፈጠር እሻለሁ›› ብሏል፡፡ እኛም እርሱ እንደ ቤተክርስቲያን ልጅነቱ ያሳየውን የፈጠራ ረቂቅ በማቅረብ ሊቃውንቱና አንባብያን ሁሉ አስተያየት በመስጠት እንዲወያዩበት የእርሱን ሐሳብ እንደሚከተለው አቅርበነዋል፤ መልካም ንባብ፡፡

Gedamate 3

የጎንደር ደብረ ኀይል ወደብረ ጥበባት በዓታ ለማርያም የአቋቋም ምስክር ትምህርት ቤት ግንባታ ውል ተፈረመ፡፡

ሚያዝያ 18/2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

Gedamate 3ማኅበረ ቅዱሳን በሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት የሚገኘውን የደብረ ኀይል ወደብረ ጥበባት በዓታ ለማርያም የአቋቋም ምስክር ትምህርት ቤትን በ4.6 ሚሊዮን ብር ለመገንባት ሚያዚያ 12 ቀን 2004 ዓ.ም. የግንባታ ውል ስምምነት ከአስማማው አያሌው ሕንጻ ሥራ ተቋራጭ ጋር ተፈራረመ፡፡ በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል አስተባባሪነት የሚከናወነው ይኸው ፕሮጀክት ማኅበረ ቅዱሳንን በመወከል የማኅበሩ ዋና ጸሐፊ ዲ/ን ሙሉጌታ ኀ/ማርያምና የሕንፃ ሥራ ተቋራጩ ባለቤትና ሥራ አስኪያጅ አቶ አስማማው አያሌው አማካይነት የፊርማ መርሐ ግብሩ ተፈጽሟል፡፡

በማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጽ/ቤት በተከናወነው የፊርማ መርሐ ግብር ላይ የማኅበሩ ዋና ጸሐፊ ዲ/ን ሙሉጌታ ኀ/ማርያም ባደረጉት ንግግር ‹‹ 4.6 ሚሊዮን ብር የሚፈጅ ፕሮጀክት ቀርጾ የአቋቋም ምስክር ትምህርት ቤት ለመገንባት ከዚህ በፊት አድርገነው አናውቅም፡፡ ይህ ትልቅ እድገት ነው፡፡ ምእመናንም ማኅበረ ቅዱሳንን ማመን የቻሉበት ነው፡፡ በሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ አውጥቶ ማኅበረ ቅዱሳን ይሥራው ለማለት መቻል ሙሉ ለሙሉ በማኅበሩ ላይ እምነት እንዳሳደሩ ነው የሚያሳየው፡፡ እኛም በታማኝነት ትኩረት ሰጥተን እንድንሠራ የሚያደርገን ነው፡፡ ጨረታውን ከብዙዎቹ የሕንጻ ሥራ ተቋራጮች ጋር ተወዳድሮ ያሸነፈው ድርጅት በማኅበሩ ውስጥ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያደረገና አብሮ የኖረ ነው፡፡ ሥራውንም በጥራትና ከተያዘለት ጊዜ ቀደም ብሎ በማጠናቀቅ ያስረክባል የሚል እምነት አለኝ፡፡ በማኅበረ ቅዱሳን በኩልም ሥራውን ለማፋጠን አስፈላጊውን ድጋፍ ሁሉ እንደሚያደርግ አረጋግጣለሁ›› በማለት ገልጸዋል፡፡

 

የሕንፃ ሥራ ተቋራጩ ባለቤትና ሥራ አስኪያጅ አቶ አስማማው አያሌው ድርጅታቸውን በመወከል እንደተናገሩት ጨረታውን ስጋበዝ አሸንፋለሁ ብዬ አላሰብኩም፡፡ የገንዘቡ መጠን ከፍ ሲል ደግሞ የማኅበረ ቅዱሳን ጓዳውን ስለማውቀው ከየት አምጥቶ ነው ብዬ ስጋት ነበረኝ፡፡ ለዚህ ደረጃ በመብቃቱ ተደስቻለሁ፡፡ ጨረታውን ለማሸነፍ ካለኝ ጉጉት የተነሣ ማግኘት ከነበረብኝ ትርፍ 7 ፐርሰንት ቀንሼ ነው የተወዳደርኩት፡፡ ለማኅበረ ቅዱሳን ገንዘብ ከመስጠት ገንዘብ መውሰድ መጀመር የጥሩ እድገት ምልክት ነው፡፡ ፕሮጀክቱን ሰርቶ ለማስረከብ ከሚጠበቀው ጊዜ በፊት እንዲሁም ከሚጠበቀው ጥራት በላይ እንደባለቤት ሰርቼ አስረክባለሁ ብለዋል፡፡

 

ሕንፃ ተቋራጩ በ1998 ዓ.ም. እንደተቋቋመና የኮንዶሚኒየም ቤቶች ግንባታዎችን፣ የአንደኛ ደረጃ ት/ቤቶች ግንባታዎችን፣ ጤና ጣቢያዎችንና በአሁኑ ወቅት የጣና በለስ ስኳር ፕሮጀክትን በ6 ሚሊዮን ብር ውል በመገንባትና በማጠናቀቅ ላይ እንደሚገኝ ጨምረው ገልጸዋል፡፡

 

በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የቦርድ ሰብሳቢ ወ/ሮ ዓለም ፀሐይ መሠረት ፕሮጀክቱን አስመልክቶ እንደገለጹት የአቋቋምGedamate 2 ምስክር ትምህርት ቤቱ ባለሁለት ፎቅ ሕንፃ ሲሆን በምስክር ትምህርት ቤቱ ውስጥ የሚገኝ ማንኛውም ተማሪ ድጋፍና ወርሃዊ ቀለብ እንዲያገኝ ማድረግ የማኅበራዊ ልማት ዋና ክፍሉ ዓላማ ነው፡፡ በተጨማሪም የአቅም ማጎልበቻ ሥልጠና፣ የስብከተ ወንጌል፣ የሐይማኖት ትምህርትና የሥራ ፈጠራ ሥልጠና በመስጠት ላይ ይገኛል፡፡ የተማሪዎቹ ማደሪያ ቤት የምግብ ማብሰያ ቤት፣ መጸዳጃ ቤትና የገላ መታጠቢያ እንዲሁም ጉባኤ ቤት የሚኖረው ሲሆን ለፕሮጀክቱ የገንዘብ ወጪውን 3.5 ሚሊዮን ብር የሸፈኑት በደቡብ አፍሪካ ነዋሪ የሆኑ 3 የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ልጆችና በጎ አድራጊዎች ሲሆኑ ፤ በአሁኑ ወቅት 1.7 ሚሊዮን ብር ለማኅበራዊ ልማት ክፍል ገቢ አድርገዋል፡፡ ቀሪውን ደግሞ ወደፊት የሚሸፍኑት ይሆናል፡፡ ተጨማሪውን ወጪ ለመሸፈን ዋና ክፍሉ የራሱን እቅድ በመቀየስ በጎ አድራጊ ምእመናንን  በማስተባበርና እንዲሳተፉ በማድረግ በጋራ ለመሥራት ነው የምናስበው ብለዋል፡፡

 

የምስክር ት/ቤቱ በአሁኑ ጊዜ ከ70 እስከ 80 ተማሪዎችን ብቻ የሚያስተናግድ ሲሆን፣  የአቋቋም ምስክር ት/ቤቱ ሲጠናቀቅ እስከ 170 ተማሪዎችን መቀበል የሚችል ነው፡፡  ተማሪዎቹ በከፍተኛ ሁኔታ የማደሪያ ቤት ችግር ስለሚያጋጥማቸው በሁለት ዓመት መጨረስ የሚገባቸው ወረፋ በመጠበቅ አራት ዓመታት ይፈጅባቸዋል፡፡ የጎጆ ወረፋ በመጠበቅ ረጅም ጊዜ ይቃጠላል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ዓላማ ያደረገው ይህንን ችግር መቅረፍ ነው፡፡ ይህ ግንባታ ዛሬ ላሉት ተማሪዎች ብቻ ትኩረት ያደረገ ሳይሆን ወደፊት ማማር ለሚፈለጉ ሁሉ ደረጃውን የጠበቀ ጉባኤ ቤቶችን መገንባት ነው በማለት ሰፊ ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡

 

የማኅበሩ መሐንዲስ የሆኑት ኢንጂነር ያሬድ ደመቀ ፕሮጀክቱን በሚመለከት እንደገለጹት የአቋቋም ምስክር ትምህርት ቤቱ ለተማሪዎቹ አገልግሎት የሚሰጡ ቁሳቁሶችን የሚያሟላ ሲሆን ከእነዚህም ውስጥ በየማደሪያ ክፍሎቹ ጠረጴዛና ወንበሮች ፤ ልብስ ማስቀመጫ ቁም ሳጥኖችና አልጋን ያካትታል፡፡ ግንባታው 1 ዓመት ከ6 ወራት እንደሚፈጅ፣ ከሕንፃ ተቋራጩ ጋር ከፊርማው በኋላ ባሉት ሰባት ቀናት ውስጥ የሳይት ርክክብ እንደሚካሄድና በ14 ቀናት ውስጥ ደግሞ ግንባታውን እንደሚጀምር በውሉ ላይ መካተቱን ይህንንም ተግባራዊ ለማድረግ እየሠሩ እንደሚገኙ ገልጸዋል፡፡

 

በፊርማ መርሐ ግብሩ ላይ ከተገኙ ወንድሞችና እኅቶች በተሰጡ አስተያየቶችም ዛሬ በማኅበረ ቅዱሳን ታሪክ ታላቅ ነገር የታየበት ነው ብለዋል፡፡ ከ12 ዓመት በፊት ይህ ክፍል ሙያ አገልግሎትና ተራድኦ ክፍል እያለ ለገዳማት ጧፍ በመላክ ነው የጀመረው፡፡ ዛሬ ታላላቅ ቅዱሳት ቦታዎች ላይ በሚሊዮን በሚቆጠር ገንዘብ ወጥቶ ሥራዎችን እንድንሠራ እግዚአብሔር ስለፈቀደልን ወደ ኋላ መመለስ አንችልም፡፡ ወደፊት ከዚህ በላይ የሆኑ ፕሮጀክቶች ይጠብቁናልና ሁላችንም በእግዚአብሔር ፈቃድ ታጥቀን መነሣትና መተባበር ይገባናል፡፡  ገጽታችን ገዘፍ እያለ ሲመጣ ጠላት ይደነግጣል፡፡ ክፉ ለሚያስቡልን ደግ እንዲያስቡ አቅም የሚፈጥር ነው፡፡ በጎ ተጽእኖ መፍጠር ያስችላል በማለት አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡

 

ይህ ፕሮጀክት 2ኛው ዙር የአብነት ት/ቤቶች በተለይም የምስክር ት/ቤቶችን ትኩረት ያደረገ መርሐ ግብር ሲሆን በመጀመሪያው ዙር የቅድስት ቤተልሔም የመጻሕፍትና የጉባኤ ቤት ተገንብቶ አገልግሎት በመስጠት ላይ እንደሚገኝ ይታወሳል፡፡

“አብዝቶ የመመገብ ጣጣው”

(በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ)

ግንቦት 30/2003 ዓ.ም.

ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ

መግቢያ

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የዮሐንስን ወንጌል በተረጎመበት በ21ኛው ድርሳኑ “ ጌታችን በእናታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ጥያቄ በቃና ሰርግ ላይ ስለምን ውሃውን ወደ ወይን ጠጅነት እንደቀየረው  ከአብራራ በኋላ ከዛሬ 1500 ዓመት በፊት በአሁኑ ጊዜ እንደ አዲስ ግኝት ተደርገው የሚታዩትን አብዝቶ በመመገብ የሚመጡትን የጤና ጉድለቶች ጽፎልን እናገኛለን ፡፡ ጽሑፉ ተተርጉሞ እንዲህ ቀርቦአል።


ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ውሃውን ወደ ወይን ጠጅነት ያኔ እንደቀየረ ዛሬም እኛን ድካማችንንና እንደ ወራጅ ውሃ በአንድ ቦታ ጸንቶ መቆየት የተሣነውን የሥጋ ፈቃዳችንን ከመቀየር አልተቆጠበም ፡፡ ዛሬም አዎን ዛሬም ልክ እንደ ወራጅ ውሃ ቀዝቃዛ ፣የፈጠነና ፣ ያልተረጋጋ ጠባይ ያላቸው ሰዎች አሉ ፡፡ እነዚህን ፈቃዶቻችንን ወደ ጌታችን እናምጣቸው ፤ እርሱ ወደ ወይንነት ይቀይራቸዋል፡፡ ከዚያም በኋላ ውኃ ሆነው ከእንግዲህ አይቀጥሉም ፡፡ ነገር ግን ለራሳቸውና ለሌሎች ደስታን የሚሰጡ አካላት ይሆናሉ ፡፡

ባልተረጋጋ ውሃ የተመሰሉት እነማን ናቸው ? ለዚህ ከንቱ ዓለም ሕሊናቸውን ያስገዙ ወገኖች ፣ የዚህን ዓለምን ቅምጥልነት ፣ አለቅነትንና ክብርን የሚሹ ናቸው፡፡ እነዚህ ፍቃዶቻችን እንደውኃ የሚፈሱ ፣ ፈጽሞ ያልተረጋጉ ፣ ለአመፃ የሚፋጠኑ ቁልቁል የሚምዘገዘጉ ውኆች ናቸው ፡፡

 

ዛሬ ሀብታም የነበረው ነገ ደሃ ይሆናል ፡፡ በአንድ ወቅት ዝናው ሲነገርለት፣ የተጌጠና የተንቆጠቆጠ ልብስ ለብሶ በሰረገላ ላይ የሚሄድና ብዙ አጃቢዎች የነበሩት ሰው ፣ ያለፈቃዱ ያን የተዋበ መኖሪያውን ተቀምቶ ወደ ወይኒ ተጥሎ ይገኛል ፡፡ ለሥጋው ደስታ የሚተጋው ሆዳሙ ደግሞ የሥጋ ፈቃዱን ከሞላ በኋላ ሆዱ ሳይጎድልበት ለአንድ ቀን መቆየት አይቻለውም ፡፡ ነገር ግን እነዚህ ምግቦች ከሆዱ ሲጠፉ ወደ ቀድሞው ምቾቱ ለመመለስ ሲል ከፊት ይልቅ አብዝቶ ይመገባል ፡፡ አመጋገቡም ሁሉን ጠራርጎ እንደሚበላ እንደጎርፍ ውሃ ነው ፡፡ በዝናብ ወቅት የሚነሣው ጎርፍ አስቀድሞ የነበረ ውሃ በከፈተለት ጎዳና ገብቶ ቦታውን ሁሉ ያጥለቀልቀዋል ፡፡ እንዲሁ በሆዳሙም ዘንድ እንዲህ ይሆናል ፡፡ አስቀድሞ የነበረው ሲጠፋ እርሱ በቀደደው ሌሎች  የሥጋ ፍቃዶች በዝተው ይገባሉ ፡፡

 

ምድራዊው ነገር ይህን ይመስላል ፤ መቼም ቢሆን የተረጋጋ አይደለም ፡፡ መቼም ቢሆን አንዱ ሌላውን እየተካ የሚፈስ እና የሚቸኩል ነው ፡፡ ነገር ግን የቅምጥልነትን ኑሮ በተመለከተ ጣጣው በከንቱ መባከን ወይም መቻኮል ብቻ አይደለም ፡፡ ሌሎችም እኛን ከመከራ የሚጥሉን ችግሮችም አሉበት ፡፡ ቅምጥልነት ባመጣብን ጣጣ የሰውነት አቅማችን ይዳከማል ፣ እንዲሁም የነፍስ ጠባይዋም ይለወጣል ፡፡ ከባድ ጎርፍ ወንዙን በደለል ወዲያው እንደማይሞላው  ፣ ቀስ በቀስ ግን እንዲሞላው ፣ እንዲሁ ቅምጥልነትና ዋልጌነት እንደ አልማዝ ብርቱ የሆነውን ጤንነታችንን ቀስ በቀስ ውጦ ያጠፋዋል ፡፡

 

ወደ ሐኪም ዘንድ ሄደህ ብትጠይቅ የበሽታዎች ሁሉ ምንጫቸው አብዝቶ ከመመገብ እንደሚመነጩ ይነግሩሃል ፡፡ ጠግቦ አለመብላትና ለሆድ የማይከብዱ ምግቦችን መመገብ ለጤንነት እናት ነው ፡፡ ስለዚህም የሕክምና ባለሙያዎች የጤንነት እናት ብለው ይጠሩታል ፡፡ እናም ጠግቦ አለመብላት የጤንነት እናት ከሆነ  ፣ አብዝቶ መመገብ ደግሞ የበሽታዎች ሁሉ እናት እንደሆነ በዚህ ይታወቃል፡፡ አብዝቶ መመገብ ሰውነታችንን አዳክሞ በሕክምና ባለሙያ እንኳ ለማይድን በሽታ አጋልጦ ይሰጠናል ፡፡

 

አብዝቶ መመገብ ለሪህ ፣ ለአእምሮ ውስጥ የደም መፍሰስ ፣ ለዐይን የማየት ኃይል መቀነስ ፣ ለእጅ መዛል ፣ ለአካል ልምሾነት  ፣ ለቆዳ መንጣት (ወደ ቢጫነት መቀየር  ፤ በተለምዶ የጉበት በሽታ ለምንለው ምልክት ነው ተብሎ ይታመናል ) ስጉና ድንጉጥ መሆን ፣ ለኃይለኛ ትኩሳት እና ከጠቀስናቸው በላይ ለሆኑ ሌሎች ሕመሞች ያጋልጣል ፡፡ በዚህ የሚመጡትን የጤንነት ጠንቆች በዚች ሰዓት ውስጥ ዘርዝሮ ለመጨረስ ጊዜው አይበቃም ፡፡ እነዚህ ሁሉ ሕመሞች በተፈጥሮአችን ላይ የሚከሰቱት መጥኖ በመብላት ወይም በጾም አይደለም ፡፡ ነገር ግን ከሆዳምነታችንና ከአልጠግብ ባይነታችን የተነሣ የሚመጡብን ናቸው ፡፡ በእነዚህ ምክንያቶች የተነሣ በነፍሳችን ላይ የሚከሰቱብንን  በሽታዎች ብንመለከት ዋዘኝነት ፣ ስንፍና ፣ ድንዛዜ ፣ የሥጋ ፍትወቶቻችን ማየል፣ እነዚህንና የመሳሰሉ ሕመሞች ነፍሳችንን ያጠቁዋታል ፡፡ ለእነዚህ ሁሉ ምንጫቸው ሳይመጥኑ አብዝቶ መመገብ ነው ፡፡ ከእንዲህ ዐይነት ቅጥ ያጣ አመጋገብ  በኋላ የቅምጥሎች ነፍስ ክፉ አውሬዎች ሥጋዋን ተቀራምተው ከተመገቡዋት አህያ ያልተሻለች ትሆናለች ፡፡ ቅምጥሎችን ስለሚጠብቃቸው  ሕመሞችና ስቃዮች ጨምሬ ልናገርን ? ከብዛታቸው የተነሣ ዘርዝሬ መጨረስ አይቻለኝም ፡፡

 

ነገር ግን በአንድ ማጠቃለያ አሳብ ሁሉንም ግልጽ አድርጌ ማስረዳት እፈልጋለሁ ፡፡ እንዲህ ከሚያደርጉ ከቅምጥሎች ማዕድ ማንም ደስ ብሎት አይመገብ ፡፡ አስቀድመን እንደተነጋገርነው ጾምና መጥኖ መመገብ የደስታና የጤንነት ምንጮች ሲሆኑ ያለቅጥ መመገብ ግን የበሽታና የደስታ ማጣት ሥር እና ምንጭ ናቸውና ፡፡

 

ሁሉ ነገር ከተሟላልን ፍላጎት የለንም ፡፡ ፍላጎት ከሌለ ደግሞ እንዴት ደስታን ልናገኛት እንችላለን ? ስለዚህም ድሆች ከባለጠጎች ይልቅ የተሻለ ማስተዋልና ጤና ያላቸው ብቻ አይደሉም ፣ ነገር ግን ታላቅ በሆነ ደስታ ውስጥ የሚኖሩ ጭምር ናቸው ፡፡ ይህንን ከተረዳን ከመጠጥና ከቅምጥልነት ሕይወት ፈጥነን እንሽሽ ፣ ከማዕዱ ብቻ አይደለም ፣ ከዚህ ሕይወት ከሚገኙት ፍሬዎች ሁሉ እንሽሽ ፡፡  እነርሱን በመንፈሳዊ ሕይወት በሚገኘው ደስታ ለውጠን በቅድስና እንመላለስ  ፡፡ ነቢዩ “ በእግዚአብሔር ደስ ይበላችሁ እርሱ የልብህን  መሻት ይሰጥሃል”(መዝ.36፥4)  እንዳለው በጌታ ደስ ይበለን ፡፡ በዚህም ዓለም በሚመጣውም ዓለም በእርሱ በእግዚአብሔር መልካም ስጦታ ደስ ይለን ዘንድ የሰው ልጆችን በሚያፈቅረው በኩል ለእርሱ ለእግዚአብሔር አብ ለመንፈስ ቅዱስም ክብር ይሁን  እስከዘለዓለሙ ፡፡ አሜን !!

 

በነገራችን ላይ የሕክምና ባለሙያዎች እንዲሁም የፍልስፍና ምሁራን(ተማሪዎች) በዚህ በቅዱስ ዮሐንስ ገለጻ ላይ ምን ይላሉ ? በ mkwebsitetechnique@gmail.com ጻፉልን።

 

begana

ማእከሉ የበገና ደርዳሪዎችን አስመረቀ

ማእከሉ የበገና ደርዳሪዎችን አስመረቀ
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ የማኅበረ ቅዱሳን የልማት ተቋማት አስተዳደር የአቡነ ጎርጎርዮስ የአብነትና የዜማ መሣሪያዎች ትምህርትና ሥልጠና ማእከል ለስድስት ወራት በበገና ድርደራ ያሰለጠናቸውን ከ175 በላይ የሚሆኑ የበገና ደርዳሪዎች መጋቢት 29 ቀን 2004 ዓ.ም. በቤተ ክህነት አዳራሽ አስመረቀ፡፡
የትምህርት ማእከሉ ሥራ አስኪያጅ የሆኑት አቶ አብዮት እሸቱ ባደረጉት ንግግር ማእከሉ ሲቋቋም በ1996 ዓ.ም. በ12 ተማሪዎች ትምህርቱን እንደጀመረና በአሁኑ ወቅት በርካታ ተማሪዎችን አቅፎ እያስተማረ እንደሚገኝ፣ በአሳሳቢ ሁኔታ እየቀነሰ የመጣውን የበገና ደርዳሪዎች ቁጥር በመጨመር ረገድ የአባቶቻችንን አሻራ ለተተኪ ትውልድ ለማስተላለፍ ማእከሉ ከፍተኛ ጥረት በማድረግ ላይ መሆኑንና በቀጣይነትም በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች ለማስፋፋት እቅድ እንዳለው ገልጸዋል፡፡
የበገና ድርደራ ሥልጠናውን ወስዶ በእለቱ ከተመረቁት ወጣቶት መካከል ወጣት ሔኖክ መንግሥቱ ለስድስት ወራት ትምህርቱን እንደተከታተለና “በመማሬ ብዙ ተጠቅሜያለሁ፤ ሥርዐተ ቤተ ክርስቲያንን የጠበቀ መዝሙር እንዳውቅ አድርጎኛል፡፡ ከዚህም ባለፈ ቤተ ክርስቲያን የምትጠቀምባቸው የዜማ መሣሪያዎች የትኞቹ እንደሆኑ፤ በግል ሕይወቴም ትሕትናንና ትእግስትን በመላበስ በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ጥሩ ሥነ ምግባር እንዲኖረኝ አድርጎኛል” በማለት ገልጿል፡፡
በዕለቱም ብጹዐን ሊቃነ ጳጳሳት፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ የተመራቂ ቤተሰቦች ጥሪ የተደረገላቸው ተጋባዥ እንግዶችና የቅዱስ ዳዊት የበገና ቤተሰብ አባላት ተገኝተዋል፡፡
ሚያዝያ 13 ቀን 2004 ዓ.ም.
በእንዳለ ደምስስ

 

 

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ የማኅበረ ቅዱሳን የልማት ተቋማት አስተዳደር የአቡነ ጎርጎርዮስ የአብነትና የዜማ መሣሪያዎች ትምህርትና ሥልጠና ማእከል ለስድስት ወራት በበገና ድርደራ ያሰለጠናቸውን ከ175 በላይ የሚሆኑ የበገና ደርዳሪዎች መጋቢት 29 ቀን 2004 ዓ.ም. በቤተ ክህነት አዳራሽ አስመረቀ፡፡
begana
የበገና ድርደራ ሥልጠናውን ወስዶ በእለቱ ከተመረቁት ወጣቶት መካከል ወጣት ሔኖክ መንግሥቱ ለስድስት ወራት ትምህርቱን እንደተከታተለና “በመማሬ ብዙ ተጠቅሜያለሁ፤ ሥርዐተ ቤተ ክርስቲያንን የጠበቀ መዝሙር እንዳውቅ አድርጎኛል፡፡ ከዚህም ባለፈ ቤተ ክርስቲያን የምትጠቀምባቸው የዜማ መሣሪያዎች የትኞቹ እንደሆኑ፤ በግል ሕይወቴም ትሕትናንና ትእግስትን በመላበስ በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ጥሩ ሥነ ምግባር እንዲኖረኝ አድርጎኛል” በማለት ገልጿል፡፡

 

የትምህርት ማእከሉ ሥራ አስኪያጅ የሆኑት አቶ አብዮት እሸቱ ባደረጉት ንግግር ማእከሉ ሲቋቋም በ1996 ዓ.ም. በ12 ተማሪዎች ትምህርቱን እንደጀመረና በአሁኑ ወቅት በርካታ ተማሪዎችን አቅፎ እያስተማረ እንደሚገኝ፣ በአሳሳቢ ሁኔታ እየቀነሰ የመጣውን የበገና ደርዳሪዎች ቁጥር በመጨመር ረገድ የአባቶቻችንን አሻራ ለተተኪ ትውልድ ለማስተላለፍ ማእከሉ ከፍተኛ ጥረት በማድረግ ላይ መሆኑንና በቀጣይነትም በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች ለማስፋፋት እቅድ እንዳለው ገልጸዋል፡፡

begena graduate

በዕለቱም ብጹዐን ሊቃነ ጳጳሳት፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ የተመራቂ ቤተሰቦች ጥሪ የተደረገላቸው ተጋባዥ እንግዶችና የቅዱስ ዳዊት የበገና ቤተሰብ አባላት ተገኝተዋል፡፡

 

የቅዱስ ያሬድ ድርሰት በሆነው ምዕራፍ ላይ ጥናታዊ ጽሑፍ ቀረበ

ሚያዝያ 13 ቀን 2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

‹‹በቅዱስ ያሬድ የዜማ አስተምህሮ የምዕራፍ ሚናና አጠቃቀም›› በሚል ርዕስ ጥናታዊ ጽሑፍ ቀረበ፡፡ በማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማዕከል አስተባባሪነት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሥርዓተ ትምህርትና የመምህራን ሙያ ልማት ትምህርት ክፍል ረዳት ፕሮፌሰርና የያሬድ ሙዚቃ ትምህርት ቤት መምህር  በሆኑት ዶክተር ውቤ ካሣዬ አማካይነት በኢትዮጵያ ብሔራዊ ሙዚየም ትልቁ አዳራሽ ቅዳሜ መጋቢት 29/2004 ዓ.ም. ቀርቧል፡፡ የጥናቱ አላማ ስለ ምዕራፍ ጠቀሜታና ክፍሎች መጠነኛ ትንታኔ መስጠት፤ ቅኝት ማድረግ፤ የቅዱስ ያሬድ የዜማ ስልቶችን ታዳሚው ግንዛቤ እንዲኖረው ማድረግና ወደፊት ሊሻሻሉ የሚገባቸው ጉዳዮች ላይ ሃሳብ ማቅረብ እንደሆነ ገልጸው፤ ነገር ግን ጥናቱ ብዙ የሚቀረው ነገር እንዳለው ጨምረው ተናግረዋል፡፡

 

ምዕራፍ የዘወትርና የጾም ተብሎ በሁለት እንደሚከፈል የገለጹት ዶክተር ውቤ ካሣዬ፤ የዘወትር የሚባለው አመቱን ሳይጠብቅ በየአመቱ ባሉት ሳምንታትና በዓላት በአገልግሎት ላይ የሚውል ሲሆን፤ የጾም ምዕራፍ ደግሞ በጾመ አርባና በአንዳድ የምህላ ቀናት እንደሚዜም፤ የሁለቱም መሠረታቸው የዳዊት መዝሙርና ድጓ ወይም ጾመ ድጓ እንደሆነ አብራርተዋል፡፡

 

በአገልግሎት ላይ ምዕራፍ ሦስት አካላት ማለትም መሪና ተመሪ እንዲሁም አንሺ ያስፈልጉታል፡፡በግራና በቀኝ በመከፋፈልና በመቀባበል ይቀርባል፡፡ ምዕራፍ በዋናነት የሚያካትታቸው ሰባት ክፍሎች አሉት፡፡ እነሱም ውዳሴ ማርያም፤ መስተጋብእ፤ አርባዕት፤ አርያም፤ ሠለስት፤ ክስተትና መወድስ በመባል ይታወቃሉ፡፡ የየራሳቸው ባህርያትና መጠን እንዳላቸውም በጥናቱ ላይ የቀረበ ሲሆን እያንዳንዱ ክፍል ከሰኞ እስከ እሁድ በመከፋፈል አቅርበውታል፡፡የድጓ መምህር በሆኑት በመምህር መንግሰቱ መላኩ/ የጥናቱ አቅራቢ የአብነት መምህር / አማካኝነት ከእያንዳንዱ ክፍል በዜማ እንዲቀርብ ተደርጓል፡፡

 

ምዕራፍ ማለት ማረፊያ ማለት ሲሆን በዜማ ቤት ሲሆን ደግሞ ከሰላም ለኪ ጀምሮ የጾም ምዕራፍ እስኪፈጸም ድረስ ያለው ትምህርት ሁሉ ምዕራፍ ይባላል፡፡ የሚጠናው በቃል ነው፡፡ በቃል ትምህርት ጊዜ የተለየ አቀማመጥ ሲኖረው በመጽሐፉ ደግሞ የተለየ ተራ እንዳለው በጥናታቸው አቅርበዋል፡፡

 

የቅዱስ ያሬድ ዜማ እጅግ የመጠቀና ሰማያዊ ምስጋና መሆኑን፤  እግዚአብሔርም ለቅዱስ ያሬድ የሰጠው የተለየ ሰማያዊ ምስጢር እንደሆነ፤  ቅዱስ ያሬድ ብቻ ሳይሆን ሌሎችም አባቶች አስተዋጽኦ እንዳደረጉ፤ ከእነዚህም  መካከከል አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫና ሌሎችም እንደሚጠቀሱ  በጥናቱ ላይ ተብራርቷል፡፡ ቅዱስ ያሬድ ከሌላው አለም የዜማ አቀራረብ ጋር ሲነጻጸር ቀደምት የሚያደርገው ሲሆን የኖታ አጠቃቀምን በተመለከተ በአለም ላይ እየተሰራበት ካለው የሙዚቃ ኖታ ፍጹም የተለየ ያደርገዋል፡፡ የቅዱስ ያሬድን የኖታ አጠቃቀም አውሮፓውያን በራሳቸው የኖታ ሥርዓት ለመቀየር ጥረት ቢያደርጉም እንዳልተሳካላቸው በጥናቱ ላይ ተገልጸል፡፡

 

የቅዱስ ያሬድን መንፈሳዊ ድርሰቶች እጅግ እንደሚመስጣቸውና ልዩ ትኩረት እንዲሰጡት እንዳደረጋቸው የገለጹት ዶክተር ካሣዬ የቅድስት ቤተክርስቲያንን የአብነት ትምህርት ለመማር ካላቸው ፍላጎት የተነሳ የቅዱስ ያሬድን ዜማ በመማር ላይ እንደሚገኙና አራት አመታትን እንዳስቆጠሩ፤ ለጥናቱም እንዳነሳሳቸው ተናግረዋል፡፡ ከዚህ ቀደም በተለያዩ የውጭ ሃገር ጸሐፍት የቅዱስ ያሬድ መንፈሳዊ ሥራዎች ላይ ጥናቶች የተደረጉ ቢሆንም ስራዎቻቸው በአብዛኛው የተዛቡ አቀራረቦች እንዳሏቸውና ለአንዳንዶቹም ማስተካከያ እንዲያደርጉ ጭምር እንደጻፉላቸውና ይህ ጉዳይ እጅግ ያስጨንቃቸው እንደነበር ገልጸዋል፡፡ ከውጭ ጸሐፍት በተጨማሪ በጣት የሚቆጠሩ የቤተክርስቲያን አባቶችና ምሁራን በቅዱስ ያሬድ ሥራዎች ላይ ጥናቶችን ያደረጉ ሲሆን፤ በአንዳንድ አባቶች ጥናት መሠረት ያሬዳዊ ዜማ በአጠቃላይ እስከ አሥራ አራት ሺህ የሚደርሱ ዜማዎች እንዳሉት ይገልጻሉ፡፡ ነገር ግን በእለቱ በመድረክ ላይ ከተጋበዙት ሊቃውንት መካከል የድጓ ሊቅ የሆኑት ሊቀ ህሩያን በላይ መኮንን ሁለተኛ ዲግሪያቸውን በመሥራት ላይ የሚገኙ ሲሆን ያሬዳዊ ዜማን አስመልክቶ ባጠኑት ጥናት መሰረት ዜማዎቹ እስከ ሃያ ሺህ እንደሚደርሱ መስክረዋል፡፡

 

በዶክተር ውቤ ካሣዬ ትኩረት ሊሰጥባቸው ይገባል ተብለው ከቀረቡ ሃሳቦች መካከል፤ የቅዱስ ያሬድ መንፈሳዊ ሥራዎች ለአለም ቅርስነት ለማስመዝገብ ጥረት ቢደረግ፤ ትውልዱን በመንፈሳዊ እውቀት ለመቅረጽ እንዲቻል በየሰ/ት/ቤቶች ትምህርቱ ቢሰጥ፤ ጥናትና ምርምር መደረግ ስለሚገባው ቤተክርስቲያን ከፍተኛ የእውቀት ክምችት ያላትና የበለጸገች ስለሆነች ይህንንም በጥናትና ምርምር በመደገፍ ማኅበረ ቅዱሳን አጠናክሮ እንዲገፋበት አሳስበዋል፡፡

 

እስከአሁንም በቤተ ክርስቲያናችን በቅዱስ ያሬድ ላይ ከጻፉ ሊቃውንት መካከል “የኢትዮጵያ ጥንታዊ ትምህርት” በሊቀ ሥልጣናት ሀብተ ማርያም ወርቅነህ፣ “ያሬድና ዜማው” በሊቀ ካህናት/ርዕሰ ደብር ጥዑመ ልሳን ካሳ፣ “ጥንታዊ ሥርዐተ ማኅሌተ ዘአቡነ ያሬድ ሊቅ” በመሪጌታ ልሣነ ወርቅ ገ/ጊዮርጊስ ይጠቀሳሉ፡፡

 

መርሃ ግብሩን በመምራት ቀሲስ ዶክተር ሙሉጌታ ስዩም በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የኢትየጵያ ቋንቋዎችና ባህሎች ት/ክፍል ረዳት ፕሮፌሰርና የማኅበረ ቅዱሳን ሥራ አመራር ሰብሳቢ የተሳተፉ ሲሆን ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ሰሙነ ሕማመትን አስመልክቶ ከቅዱስ ያሬድ ዝማሬዎች በመርሐ ግብሩ መጀመሪያና መዝጊያ ላይ አቅርበዋል፡፡ በመርሐ ግብሩ ላይ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ መምህራን፤ ከተለያዩ ተቋማትና መሥሪያ ቤቶች ጥሪ የተደረገላቸው ኃላፊዎችና ምዕመናን የተገኙ ሲሆን በቀረበው ጥናት ላይ  ከታዳሚዎች ለቀረቡ ጥያቄዎች በጥናቱ አቅራቢ ምላሽ ተሰጥቷል፡፡

የትንሣኤው ትርጉም በዓሉና አከባበሩ

ከሊቀ ትጉሃን ኀ/ጊዮርጊስ ዳኘ
በጠ/ቤተ ክህነት የዕቅድና ልማት መምሪያ ምክ/ሓላፊ

  • «ትንሣኤ» የሚለው ቃል የግእዝ ቋንቋ ነው፡፡

  •  መገኛ ቃሉም «ተንሥአ» = ተነሣ የሚለው ግሥ ይሆናል፡፡

  • «ትንሣኤ» ማለት ታዲያ = መነሣት፣ አነሣሥ ሐዲስ ሕይወት ማግኘት ማለትን ያመለክታል፡፡

  •  «ትንሣኤ» በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን በየመልኩ፣ በየዐይነቱ ሲተረጐም ዐምስት ክፍል አለው፡፡

  • «ትንሣኤ» የሚለው ቃል የግእዝ ቋንቋ ነው፡፡

  • መገኛ ቃሉም «ተንሥአ» = ተነሣ የሚለው ግሥ ይሆናል፡፡

  • «ትንሣኤ» ማለት ታዲያ = መነሣት፣ አነሣሥ ሐዲስ ሕይወት ማግኘት ማለትን ያመለክታል፡፡

  • «ትንሣኤ» በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን በየመልኩ፣ በየዐይነቱ ሲተረጐም ዐምስት ክፍል አለው፡፡

  • አንደኛው «ትንሣኤ» ኅሊና ነው፡፡ ይህም ማለት ተዘክሮተ እግዚአብሔር ነው፡፡

  •  ሁለተኛውም «ትንሣኤ» ልቡና ነው፡፡ የዚህም ምስጢሩ ቃለ እግዘብሔርን መስማትና በንስሐ እየታደሱ በሕይወት መኖር ነው፡፡

  •  ሦስተኛው «ትንሣኤ» ለጊዜው የሙታን በሥጋ መነሣት ይሆናል፡፡ ነገር ግን ድጋሚ ሞት ይከተለዋል፡፡

  • አራተኛው «ትንሣኤ» የክርስቶስ በገዛ የባሕርይ ሥልጣኑ ሞትን ድል አድርጎ መነሣት ነው፡፡ የእርሰ ትምህርታችንም መሠረት ይኸው እንደሆነ ይታወሳል፤ ብለን ተስፋ አናደርጋለን፡፡

  • ዐምስተኛውና የመጨረሻው «የትንሣኤ» ደረጃም የባሕርይ አምላክ የጌታችን የመድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን «ትንሣኤ» መሠረት ያደረገ «ትንሣኤ ዘጉባኤ» ነው፡፡ ይህም ከዓለም ኅልፈት በኋላ ሰው ሁሉ እንደየሥራው ለክብርና ለውርደት፣ ለጽድቅና ለኩነኔ በአንድነት የሚነሣው የዘለዓለም ትንሣኤ ይሆናል፡፡

  • ወደተነሣንበት ዐላማ ስንመለስ የትንሣኤ በዓል በቃሉም ምስጢር በይዘቱም ስለሚመሳሰሉ ጥላው ምሳሌውም፣ ስለሆነ «ፋሲካ» ተብሎ ይጠራል፡፡

  • «ፋሲካ» ማለት በዕብራይስጥ ቋንቋ «ፌሳሕ» በጽርእ በግሪክኛው «ስኻ» ይባላል፡፡ ይህም ወደ እኛው ግእዝና ዐማርኛ ቋንቋችን ሲመለስ ፍሥሕ ዕድወት = ማዕዶት፣ በዓለ ናእት = የቂጣ በዓል፣ እየተቸኮለ የሚበላ መሥዋዕት፣ መሻገር መሸጋገር ማለት ነው፡፡ ነጮቹ በእንግሊዝኛው «ስኦቨር» ይሉታል የዚህም ታሪካዊ መልእክቱ በዘመነ ኦሪት ይከበር የነበረው በዓለ ፋሲካ እስራኤል ዘሥጋ ከግብጽ የባርነት ቀንበር ወደነፃነት የተላለፉበት፣ ከከባድ ሐዘን ወደ ፍጹም ደሰታ፣ የተሸጋገሩበት በዓል ነበር፡፡ በዚህ ኦሪታዊ ምሳሌ በዓል አሁን አማናዊው በዓል «ትንሣኤ» ተተክቶበታል፡፡

  • ፋሲካ፣ በዓለ ትንሣኤ በዘመነ ሐዲስ እስራኤል ዘነፍስ የሆኑት ምእመናነ ክርስቶስ ትንሣኤውን የሚያከብሩበት ዕለት ሆኖ በእርሱ ትንሣኤ

  • ከኀጢአት ወደ ጽድቅ፣

  • ከኀሳር = ከውርደት ወደክብር፣

  • ከጠላት ሰይጣን አገዛዝ ወደ ዘለዓለማዊ ነፃነት፣

  • ከአደፈ፣ ከጐሰቆለ አሮጌ ሕይወት ወደ ሐዲሰ ሕይወት የተሻገሩበት ታላቅ መንፈሳዊ የነፃነት በዓል ነው፡፡

– ክርስቲያኖች የትንሣኤን በዓል በታላቅ ደስታና መንፈሳዊ ስሜት ያከብሩታል፡፡ ስለዚህም ከበዓላት ሁሉ የበለጠ ሆኖ ይታያል፡፡
– መድኀኒታችን ሞትን በሞቱ ድል መትቶ፣ ስሙና መቃብርን አጥፍቶ በሥልጣኑ የተነሣው መጋቢት 29 ቀን በ34 ዓ.ም እንደሆነ ታሪከ ቤተ ከርስቲያን ያስረዳል፡፡
– የትንሣኤ በዓል መከበር የጀመረው በቅዱሳን ሐዋርያትና በሰብዐ አርድእት፣ ኋላም በየጊዜው በተነሡት ተከታዮቹ ምእመናን ነው፡፡ ድምቀቱና የአከባበር ሥርዐቱ ይበዛ ይቀነስ እንደሆን እንጂ መከበሩ ተቋርጦ አያውቅም፡፡ «እንኳን ለብርሃነ ትንሣኤው አደረሰን»
– ሲወርድ ሲወራረድ ከዚህ በደረሰው ትውፊት መሠረት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ግብረ ሕማማቱን ስታነብ ሰንብታ ለትንሣኤ እሑድ አጥቢያ ማታ በ2 ሰዓት «ለጸሎት ተሰብሰቡ» የደወል ድምፅ ታሰማለች፡፡

– ካህናቱ ተሰብስበው ሥርዐቱን በጸሎት ይጀምራሉ፡፡ ሕዝቡም ይሰበሰባል፡፡ ቤተ ክርስቲያኑንም ይሞላዋል፡፡

– ካህናቱ ሁሉ ለጸሎተ ፍትሐትም፣ ለሥርዐቱም መዝሙረ ዳዊት፣ ነቢያት፣ ሰሎሞንና ውዳሴ ማርያም ከደገሙ በኋላ «ተፈሥሒ ማርያም ለአዳም ፋሲካሁ» የሚለውን ግጥማዊ የደስታ መዝሙር ይዘምራሉ፡፡
– ቀጥሎም ምንባባቱና ሌላውም ሥርዐት ከተፈጸመ በኋላ ጸሎተ አኰቴት ተደርሶ ዲያቆኑ «ወተንሥአ እግዚአብሔር ከመ ዘንቃህ እምንዋም፣ ወከመ ኀያል ወኅዳገ ወይን፣ ወቀተለ ፀሮ በድኅሬሁ = እግዚአብሔር ከእንቅልፍ እንደሚነቃ ተነሣ፤ የወይን ስካር እንደተወው ኀያል ሰውም፣ ጠላቱን በኋላው ገደለ፡፡» የሚለውን የዳዊት መዝሙር ለመስበክ = ለመዘመር ነጭ ልብሰ ተክህኖ ለብሶ አክሊል ደፍቶ፣ የመጾር መስቀል ይዞ፣ እንደእርሱው ነጭ ልብሰ ተክህኖ በለበሱ ደማቅ የጧፍ መብራት በሚያበሩና ድባብ = ጃንጥላ በያዙ ሁለት ዲያቆናት በግራ በቀኝ ታጅቦ ከመቅደስ ብቅ ብሎ በቅድስት ይቆማል፡፡ መዝ. 77-65 ይህም በጌታችን መቃብር በራስጌና በግርጌ በታዩት መላእክት ምሳሌ ነው፡፡ ዮሐ.20-12
– ዲያቆኑ ከላይ የተጠቀሰውን ምስባክ በረጅም ያሬዳዊ ዜማ በሰበከ ጊዜ ካህናቱ ከበሮ እየመቱና በእርጋታ እያጨበጨቡ ተቀብለው ይዘምራሉ፡፡

– ሕዝቡም የቻለው በዝማሬው ያለበለዚያም በጭብጨባና በልልታ የደስታ ዝማሬው ተሳታፊ ይሆናል፡፡ ይህ ምስባኩ በዲያቆኑ 2 ጊዜ በመላው ካህናትም 2 ጊዜ ለመጨረሻ ጊዜ ዲያቆኑም መላው ካህናትም አንድ ጊዜ ብለው 5 ጊዜ ይሆናል፡፡ 5500 ዘመን ሲፈጸም በጌታችን ሞትና ትንሣኤ ዓለም ለመዳኑ ምሳሌያዊ ማስረጃ ነው፡፡

– ቀጥሎም ካህኑ ትንሣኤውን የሚያበሥር ወንጌል ከማቴዎስ፣ ከማርቆስና ከሉቃስ አውጥቶ ያነባል፡፡ ከዮሐንስ ወንጌል ያለው የትንሣኤው ወንጌል ኋላ ለቅዳሴው ጊዜ ይቆያል፡፡ ዮሐ. 20-1-09
– በማስከተል የዲያቆኑን መስቀል ጨብጦ ከሊቃውንቱ መዘምራን ሥራው የሚመለከተው ወይም የተመደበው ባለሙያ መዘምር «ትንሣኤከ ለእለ አመነ» የሚለውን እስመ ለዓለም ከቃኘ በኋላ ለበዓሉ ተስማሚ የሆነው 2 አርያም ተመርቶ በመቋሚያ ይዘመማል፤ በማስከተልም «ዮም ፍሥሐ ኮነ በሰንበተ ክርስቲያን፣ እስመ ተንሥአ ክርስቶስ እሙታን = ክርስቶስ ከሙታን ቀድሞ ተለይቶ ተነሥቷልና በሰንበተ ክርስቲያን ዛሬ ደስታ ሆነ፡፡…» የሚለውን አንገርጋሪ ያመለጥናል = ይመራል፡፡ በግራ በቀኝ እየተነሣ መዘምራኑም ይዘምሙታል ይጸፉታል፤ ያለዝቡታል፤ ወዲያውም «ብርሃነከ ፈኑ፤ ለእለአመነ = ለአመነው ብርሃንህን ላክልን፡፡» የሚለውን እስመ ለዓለም እየወረቡ መብራት እያበሩ ዑደት ያደርጋሉ = ቤተ ክርስቲያኑን በውስጥ ይዞራሉ፡፡
– በዚህ ጊዜ «በጨለማ የነበራችሁ ሕዝቦች ኑ የትንሣኤውን ብርሃን እዩ፣ ብርሃኑንም ወስዳችሁ የብርሃኑ ተካፋይ ሁኑ፡፡» እያለች ቅ/ቤተ ክርስቲያን ስታዘጋጅ የሰነበተችውን ጧፍ እያበራች ታድላቸዋለች፡፡ ሕዝቦቹም ካህናቱን ተከትለው በታላቅ ደስታና ድምቀት ዑደት ያደርጋሉ፡፡
– መዘምራኑና ካህናቱ ከዑደት ሲመለሱ «ይእቲ ማርያም» የተባለው የኪዳን ሰላም ይጸፋና ኪዳን ተደርሶ ሲያበቃ እንደ ቦታው ደረጃ ፓትርያርኩ ወይም ሊቀ ጳጳሱ ወይም ደግሞ አለቃው፣ ቆሞሱ፣ ካህኑ ዘለግ ባለ ድምፅ በንባብ «ክርስቶስ ተንሥአሙታን = ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ ተነሣ፡፡» ሲል ካህናቱና መዘምራኑ በዐቢይ ኀይል ወሥልጣን = በታላቅ ኀይልና ሥልጣን፡፡» ብለው ይቀበላሉ፡፡
– አሁንም ካህኑ «አሰሮ ለሰይጣን = ሰይጣንን አሰረው» ባለ ጊዜ መላው ካህናት «አግዐዞ ለአዳም = አዳምን ሐርነት ነጻነት አወጣው» ይላሉ፡፡ ቀጠል አድርጎ ቄሱ «ሰላም፣ ፍቅር፣ አንድነት» ሲላቸው ሁሉም ካህናት «እምይእዜሰ = ከዛሬ ጀምሮ» ብለው ይቀበላሉ፡፡ ቄሱም «ኮነ ፍሥሐ ወሰላም = ሰላምና ደስታ ሆነ» ብሎ ሦስት ጊዜ ዐውጆ ሲያበቃ «ነዋ መስቀለ ሰላም» እያለ መስቀል ሲያሳልም ካህናትና ሕዝቡም «ዘተሰቅለ ቦቱ መድኀኔዓለም» እያሉ ይሳለማሉ፡፡ ካህኑም «እግዚአብሔር ይፍታ» ይላል፡፡ ግብረ ሕማማት ሲነበብበት ከሰነበተው ጠበልም ይረጫል፡፡ የተረፈውንም ጠበል ሕዝቡ ለበረከት ወደየቤቱ ይወስደዋል፡፡
– ከዚያም ልኡካኑ ለቅዳሴ እየተዘጋጁ ሊቃውንት መዘምራኑ ምስማክ መወድሱን ካዜሙ በኋላ በመቋሚያ ይዘምሙታል፡፡ አያይዞም በዓመት ሦስት ጊዜ የሚዘመረውን «ይትፌሣሕ» የተባለውን መዝሙር ቃኝተው ከዘመሙ በኋላ «ወምድርኒ ትገብር ፋሲካ፤ ተኀፂባ በደመ ክርስቶስ = ምድርም በክርስቶስ ደም ታጥባ ፋሲካውን ታደርጋለች፡፡» እያሉ ይጸነጽላሉ፡፡ አያይዘውም የመዝሙሩን ሰላም ይጸፋሉ፡፡
– ወዲያው መንፈቀ ሌሊት ሲሆን ቅዳሴ ተቀድሶ ይቆረባል፡፡ ከዚያም ዕጣነ ሞገር = በዕጣን ፈንታ ቅኔው ተቁሞ ሠርሖተ ሕዝብ = የሕዝብ ስንብት ከሆነ በኋላ ለመፈሰክ ሕዝቡ ወደየ ቤቱ ይሔዳል፡፡
– ሕዝቡ በየቤቱ፣ ካህናቱም ከቤተ ክርስቲያን በየአካባቢው ባህል በተለይ አክፋዮች መጀመሪያ ቅባት አጥቶ የሰነበተ ሆድ እንዲለሰልስ የተሞቀ የተልባ ጭልቃ ይጠጣና የሹሮ ወጥ በቅቤ፣ በአይብ፣ የበረታም በዶሮ ወጥ፣ ወይም በበግና በከብት ሥጋ ወጥ ይገድፋል፡፡
– በእርጎ፣ በአይብ የተደራረበ እንጀራ በግፍልፍል የሚገድፉም አሉ፡፡ በአንዳንድ የሰሜኑ ሀገራችን ደግሞ የተልባ፣ የኑግና የሱፍ ጭልቃ ከማር ጋር ታሽቶ ከተጠጣ በኋላ በእርጎ፣ በአይብ፣ በወተት፣ በቅቤና ድልህ በተቀባ እንጀራ ይገድፋሉ፡፡
– ሲነጋም ከጾሙ አጋማሽ ጀምሮ ወንዱ ለእርድ የሚሆነውን ሰንጋውን፣ ሲቀልብ፣ በጉን ፍየሉን ሲሞክት ዶሮውን ሲመርጥ፣ ሲገዛ ሲለውጥ፣ ሰንብቶ ነበርና በግልም በኅብረትም ያ ይታረዳል፡፡
– ሴቶችም ቅቤውን ሲያነጥሩ፣ በርበሬውን ሲደልሁ፣ ለእንጀራና ዳቦ የሚሆነውን ዱቄት ሲያዘጋጁ ለጠላ የሚሆነውንም እኸል ሲያሰናዱ አይቡን በልዩ ልዩ ቅመም መጣጣ ሲያደርጉና ባዶ ማለትም ወገሚት የተባለውን በሽንኩርት፣ በጤና አዳም፣ ጣዕሙ እንዳይለወጥ ሲቀምሙ ሰንብተው ዝግጅቱ ተከናውኖ ነበር፡፡
– ጧትም ይህ የመግደፊያ ዝግጅት በየቤታቸው ለሌላቸው ድኾች በየመንደሩ እየተዞረ «እንኳን ጾመ ልጓሙን ፈታላችሁ» እየተባለ ከሥጋውም፣ ከአይቡም፣ ከቅቤውም ከመጣጣሙም፣ ከእርጐውም ይታደላል፡፡
– ከትንሣኤ እሑድ ጀምሮ እስከ ዳግም ትንሣኤ ድረስ ሕዝበ ክርስቲያኑ «እንኳን ጾመ ልጓሙን ፈታላችሁ» እየተባባለ በመጠራራት ዐብሮ ሲበላ ሲጠጣ ልዩ ልዩ ጨዋታ ሲጨዋወት ለንስሐ አባትና ለሽማግሌዎች ለወዳጅ ዘመድም የአክፋይ ዳቦ፣ ወይም የሥጋ ወጥ ግፍልፍል ሲወስድ ይሰነብታል፡፡
– ይህ በዚህ እንዳለ ከትንሣኤ እሑድ ቀጥለው ያሉት ዕለታት ሰሙነ ፋሲካ ወይም ትንሣኤ እየተባሉ የየራሳቸው ምስጢራዊ ስያሜ አላቸው፡፡ ይኸውም፡-
ሰኞ = ጌታችን በሞትና ትንሣኤው ነፍሳትን ከሲኦል አውጥቶ ወደ ገነት አሻግሮ ለማስገባቱ መታሰቢያ ሆና «ፀአተ ሲኦል ማዕዶት» ትባላለች፡፡ ዮሐ. 19-18 ሮሜ. 5-10-17 የዳግም ትንሣኤው ማግሥት ያለችው ግን ገበሬው፤ ወንዶቹ እርሻ ቁፋሮውን፣ ንግዱን፣ ተግባረ እዱን ሁሉ ሴቶቹ ወፍጮውን፣ ፈትሉን፣ ስፌቱን የሚጀምሩባት ዕለት ስለሆነች «እጅ ማሟሻ» ሰኞ ትባላለች፡፡
ማክሰኞ = የትንሣኤው ዕለት እሑድ ማታ ጌታችን በዝግ ቤት ገብቶ ለሐዋርያት ሲገለጽ ቶማስ ሐዋርያ አልነበረም ኋላ ከሔደበት ሲመጣ ሌሎቹ ሐዋርያት ትንሣኤውን ቢነግሩት እኔ ሳላይ አላምንም በማለቱ በዚህ ጥያቄው መሠረት በሳምንቱ ጌታችን በድጋሚ ስለተገለጸ ለዚህ መገለጹ መታሰቢያ ሆና ዕለቲቱ «በቶማስ» ተሰየመች፡፡ ዮሐ. 20-24-30
– ረቡዕ = ከሞተና ከተቀበረ አራት ቀን በኋላ ከመቃብር ጠርቶ ላሥነሣው፣ አላዓዛር መታሰቢያ የእርሱንም ተነሥቶ በማየት በጌታችን ብዙ ሕዝብ ስለአመነበት ቀኒቱ «አላዓዛር» ተብላ ትታሰባለች፡፡ ዮሐ. 11-38-46
ኀሙስ = ከላይ በጸሎተ ኀሙስ ሐተታ ላይ እንደተገለጸው የአዳም ተስፋው ተፈጽሞለት ከነልጅ ልጆቹ ወደቀደመ የገነት ክብሩ ለመግባቱ መታሰቢያ ሆና «የአዳም ኀሙስ» ተብላ ይኸው ትከበራለች፡፡ ሉቃ. 24-25-49
– ዐርብ = በክርስቶስ ደም ተዋጅታ በተመሠረተችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ታላቅ መታሰቢያ በመሆኗ በሰሙነ ፋሲካው ያለችው ዐርብ «ቤተ ክርስቲያን» ተብላ ትጠራለች፡፡ ማቴ. 26-26-29 የሐ. ሥራ. 20-28 ይህች ዕለትም እንደ ዕለተ ኀሙስ ሦስት ስያሜዎች አሏት፡፡ ይኸውም እንደኛው ከሆሳዕና ቅዳሜ በፊት ያለችው ዐርብ የጌታችን አርብዓው ጾም የሚፈጸምባት የጾመ ድጓው ቁመትም የሚያበቃባት፣ በመሆኗ በቤተ ክርስተያን «ተጽዒኖ» ስትባል በሕዝቡም ዘንድ በሕማማትና ሰሙነ ትንሣኤው ከባዱን ሥራ ስለሚያቆምባት «የወፍጮ መድፊያ፣ የቀንበር መስቀያ» ትባላለች፡፡
– ሁለተኛውም በመጀመሪያ የሰው አባትና እናት አዳምና ሔዋን ስለተፈጠሩባት፣ ኋላም በሐዲስ ኪዳን ጌታችን ለቤዛ ዓለም መከራ ተቀብሎ ስለተሰቀለባትና የማዳን ሥራውን ስለፈጸመባት «ዕለተ ስቅለት አማናዊቷ ዐርብ» ትባላለች፡፡
– ሦስተኛውም ይኸው በሰሙነ ትንሣኤው ያለችው ደግሞ «ቤተ ክርስቲያን» ትባላለች ማለት ነው፡፡
– ቀዳሚት = በሰሙነ ፋሲካው ያለችው ቀዳሚት ሕዝቡ ከአንዳንዱ በስተቀር ገበያ እንኳን ስለማይገበይባት «የቁራ ገበያ» የገበያ ጥፊያ ስትባል በቤተ ክርስቲያን ግን በዘመነ ሥጋዌው በገንዘባቸውና ጉልበታቸው ለአገለገሉት በስቅለቱ ዋይ ዋይ እያሉ እስከ ቀራንዮ ለተከተሉት፣ የትንሣኤው ዕለት ገና ከሌሊቱ ወደ መቃብሩ ሽቱና አበባ ይዘው በመገሥገሣቸው ትንሣኤው ከሁሉ ቀድሞ ለተገለጸላቸው ቅዱሳት አእንስት መልካም መታሰቢያ ሆና «አእንስት» ተብላ ትጠራለች፡፡ ሉቃ. 23-27-33፣ 24-1-01፣ ማቴ. 25-1-11
 

የዋናው ትንሣኤ ሳምንት እሑድ…

 
በዚች ሰንበት ከላይ እንደተጠቆመው የትንሣኤው ዕለት ጌታችን ለቅዱሳን ሐዋርያት በዝግ በር ገብቶ በመካከላቸው ተገኝቶ «ሰላም ለሁላችሁ ይሁን» ብሎም ትንሣኤውን ሲገልጽላቸው ሐዋርያው ቶማስ አልተገኘም ነበር፡፡ በኋላ ከሔደበት ሲመጣ የጌታችንን መነሣትና እንደተገለጸላቸው በደስታ ሲነግሩት «በኋላ እናንተ ዐየን ብላችሁ ልትመሰክሩ፣ ልታስተምሩ፣ እኔ ግን «ሰምቼአለሁ» ብዬ ልመሰክር፣ ላስተምር? አይሆንም እኔም ካላየሁ አላምንም» በማለቱ የሰውን ሁሉ፤ ይልቁንም የመረጣቸው ወዳጆቹን የልብ ሐሳብ ምክንያቱን ለይቶ የሚያውቀው፣ ቸርነቱ ወሰን የሌለው የባሕርይ አምላክ መድኀኔዓለም ክርስቶስ ልክ እንደመጀመሪያው ትንሣኤ ዕለት አበው ሐዋርያት በአንድነት በተዘጋ ቤት እንዳሉ በሩን ሳይከፍት ገብቶ «ሰላም ለሁላችን ይሁን» በማለት በመካከላቸው ቆመ፤ ቶማስንም «ያመንክ እንጂ ተጠራጣሪ አትሁን እነሆ የተቸነከሩ እጆቼንና እግሮቼን፣ የተወጋ ጐኔንም ናና እይ» ብሎ አሳየው፡፡ እርሱም ምልክቱን በማየቱ በመዳሰሱ ትንሣኤውንና አምላክነቱን እንደፍላጎቱ በመረዳቱ «ጌታዬ አምላኬ ብሎ መስክሮ» አመነ፡፡
– እንግዲህ ይህ የትንሣኤው ምስጢር ለሁለተኛ ጊዜ ለሐዋርያት የተገለጠበት ዕለት ስለሆነ «ዳግም ትንሣኤ» ተብሎ ሰንበቱ ይጠራበታል፤ ይከበርበታል፡፡ ዮሐ. 20-24-30
– በቅድስት ቤተ ክርስቲያን የሚፈጸመው መንፈሳዊና ሐዋርያዊ አገልግሎት ሁሉ ከቅዳሴው ውጭ ከሚፈጸመው «ድኅረ ቁርባን» በስተቀር ልክ እንደመጀመሪያው የትንሣኤ ዕለት ሆኖ ይከናወናል፡፡

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ለብርሃነ ዕርገቱም በሰላም ያድርሰን፡፡ አሜን!!

st.Tomas

ዳግም ትንሣኤ (ለሕፃናት)

ሚያዝያ 12/2004 ዓ.ም.

በእኅተ ፍሬስብሐት

st.Tomasጌታችን በተነሣበት ዕለት የክርስቶስ ደቀመዛሙርት ተሰብስበው ሳለ ጌታችን በመካከላቸው ቆመና “ሰላም ለእናንተ ይሁን “አላቸው፡፡ የነበሩበት ቤት በሩም መስኮቱም ተቆልፎ ስለነበር ደቀ መዛሙርቱም በጣም ደነገጡ፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም  “አትፍሩ እኔ አምላካችሁ ነኝ” ብሎ የተወጋ ጎኑን እና የተቸነከሩ እጆቹን አሳያቸው፡፡ እነርሱም ጌታ ከሞት መነሣቱን አመኑ፡፡ ደቀመዛሙርቱንም(ተማሪዎቹንም) ሕዝቡን እንዲያስተምሩ ላካቸው፡፡

በዚህ ዕለት ከ12ቱ ደቀመዛሙርት አንዱ የሆነው ቶማስ ከእነርሱ ጋር አልነበረም፡፡ ደቀመዛሙርቱ የጌታን መነሣት እና እነርሱም እነዳዩት ነገሩት፡፡ እርሱ ግን በዓይኔ ካላየሁ አላምንም አለ፡፡

 

ከስምነት ቀን በኃላ እንደገና ቶማስ አብሯቸው ሳለ በሩ እንደተዘጋ ጌታችን መጣ፣  በመካከላቸውም ቆሞ “ሰላም ለእናንተ ይሁን” አላቸው፡፡ ቶማስ ትንሣኤውን እነደተጠራጠረ ስላወቀ  እጅህን አምጣና የተወጋ ጎኔን እና የተቸነከሩ እጆቼን ዳስስ አለው፡፡ ቶማስም በዳሰሰው ጊዜ አምላክ መሆኑን ዐወቀ፡፡ ይኽ ዕለት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሁለተኛ ጊዜ ቶማስ ባለበት  ለደቀመዛሙርቱ የተገለጠበት ዕለት በመሆኑ ዳግም ትንሣኤ ተብሎ ተሰየመ፡፡ ዳግም ማለት ሁለተኛ ማለት ነው እሽ ልጆች፡፡ በሚቀጥለው ሳምንት በሌላ ታሪክ እሰክንገናኝ ደኅና ሁኑ!

የትንሣኤ ሰላምታ

yetnsaeselamta2in1


“ክርስቶስ ተንሥአ እሙታን፤ በዐቢይ ኃይል ወሥልጣን፤ አሰሮ ለሰይጣን፤ አግዐዞ ለአዳም፤ ሠላም እምይዕዜሰ፤ ኮነ፤ ፍስሐ ወሠላም፡፡”

በመ/ር ምሥጢረ ሥላሴ ማናየ

“ክርስቶስ በታላቅ ኃይልና ሥልጣን ከሙታን ተለይቶ ተነሣ ዲያብሎስን አሰረው አዳምን ነጻ አወጣው ሠላም ከዛሬ ጀምሮ ሰላም ሆነ” ይህ ቃል የትንሣኤው የምሥራች ለምእመናን የሚታወቅበት ነው የሚቀድስ ካህን፣ ሰባኪ በዘመነ ትንሣኤ ከስብከቱ አስቀድሞ በዚህ ቃል የክርስቶስን መነሣት ያውጃል፡፡ የሚቀድሰው ካህንም በኪዳን ጊዜ ህዝቡን ከመባረኩ አስቀድሞ ይህንኑ ቃል ይናገራል ሰላምታ የሚቀባበሉ ምእመናንም ሰላምታ ከመስጠት አስቀድሞ ይህን ቃል በመናገር የትንሣኤውን አዋጅ ማወጅና መመስከር ይገባቸዋል፡፡ እንኳን ለብርሃነ ትንሣኤው አደረሰን አደረሳችሁ፡፡

የክርስቶስ ትንሣኤ እንደ እንግዳ ደራሽ እንደ ውኃ ፈሳሽ አይደለም ከጥንት በነቢያት የተነገረ ኋላም እርሱ ክርስቶስ ለደቀ መዛሙርቱ ከመሞቱ አስቀድሞ ያስተማረው ደግሞም በመነሣት የገለጠው ሐዋርያትም በግልጥ ለዓለም የመሰከሩት ነው፡፡

ትንሣኤ በትንቢተ ነቢያት

“እግዚአብሔር ይነሣል ጠላቶቹም ይበተናሉ” “እግዚአብሔር ከእንቅልፍ እንደሚነቃ ተነሣ የወይን ስካር እንደተወው እንደ ኃያልም ሰው ጠላቶቹንም በኋላው መታ” መዝ.77፥6 “እኔ ተኛሁ አንቀላፋሁም እግዚአብሔር አሥነስቶኛልና ተነሣሁ” መዝ.3፥5 “እግዚአብሔር አሁን እነሣለሁ ይላል መድኀኒት አደርጋለሁ

ቅዱስ ዳዊት በዚህ መልኩ የክርስቶስን ከሙታን መነሣት ተናግሯል፡፡ እርሱን መሰል ነቢያት ክርስቶስ እንዲሞት በ3ኛው ቀን ከሙታን ተለይቶ እንደሚነሣ ገልጸዋል፡፡ ምሳሌ ተመስሏል፤ ትንቢትም ተነግሯል፤ ዮናስ ሦስት መዓልትና ሦስት ሌሊት በአሣ አንበሪ ሆድ ውስጥ እንደ አደረ ክርስቶስም ሦስት መዓልትና ሦስት ሌሊት በከርሰ መቃብር አድሮ ሙስና መቃብርን አጥፍቶ ብርሃነ መለኮቱን ገልጾ እንደሚነሣ ራሱ ባለቤቱ እግዚአብሔር ወልድ ተናግሯል፡፡ ዮና.2፥1 ማቴ.12፥4ዐ ነቢየ እግዚአብሔር ሆሴዕ “ከሁለት ቀን በኋላ ያድነናል፡፡ በሦስተኛው ቀን ያስነሣናል በፊቱም በሕይወት እንኖራለን” ሆሴ.6፥2 ብሎ የአምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ ለእኛም ትንሣኤያችን፣ ሕይወታችን መሆኑን ገልጾ ተናግሮታል፡፡ ሆሴዕ በተጨማሪም “ሞት ሆይ መውጊያህ ወዴት አለ? ሲኦል ሆይ /መቃብር/ ድል መንሳትህ ወዴት አለ?” ሆሴ.13፥14 ብሎ ሞት እና መቃብር ሥልጣናቸው እንደተሻረ ይዘው ማስቀረታቸው እንደቀረ በክርስቶስ ትንሣኤ የሰው ልጆች ትንሣኤ እንደተገለጸ ይነግረናል “ልጄ ሆይ ከመሰማሪያህ /ከመቃብር/ ወጣህ እንደ አንበሳ ተኛህ አንቀላፋህም እንደ አንበሳ ደቦል የሚቀሰቅስህ የለም” ዘፍ.49፥9 ከላይ በተመለከትነው ጥቅስ የሚቀሰቅስህ የለም የሚለው ክርስቶስ በገዛ ሥልጣኑ አስነሽ ሳይሻ የተነሣ መሆኑን ይነግረናል ይህንም ክርስቶስ በራሱ ሥልጣን እንደሚነሣ ሲያስተምር እንዲህ ይላል፡፡ “እንደገና አስነሣት ዘንድ እኔ ነፍሴን እሰጣለሁና ከእኔ ማንም አይወስዳትም ነገር ግን እኔ በፍቃዴ እሰጣታለሁ እኔ ላኖራት ሥልጣን አለኝ መልሼ እወስዳት ዘንድ ሥልጣን አለኝና” ዮሐ.10፥17 ይህ የሚያስረዳን ክርስቶስ በፈቃዱ ለዓለም ቤዛ ሆኖ እንደ ሞተ በሥልጣኑ እንደተነሣ ነው፡፡

የክርስቶስ ትንሣኤ በሐዲስ ኪዳን

አራቱም ወንጌላውያን ትንሣኤውን እንደ አንድ ልብ መካሪ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ሆነው በወንጌል ጽፈውታል፡፡ ቅዱስ ማቴዎስ በወንጌሉ ምዕራፍ 28፥1-16 በሰንበትም ማታ ለእሑድ አጥቢያ ማርያም መግደላዊትና ሁለተኛዋ ማርያም መቃብሩን ሊያዩ መጡ እነሆ ታላቅ የምድር መናወጥ ሆነ የእግዚአብሔር መልአክ ከሰማይ ወርዷልና ቀርቦም በመቃብሩ አፍ ላይ ድንጋይዋን አንከባሎ በላይዋ ተቀመጠ” ይላል በዕለተ ትንሣኤ የክርስቶስን ትንሣኤ ለማየት መላእክት እንዲሁም ቅዱሳት አንስት ተገኝተዋል ሲወለድ የመወለዱን ዜና ለዕረኞች የተናገሩ መላእክት በትንሣኤው ዕለትም ዜና ትንሣኤውን ለቅዱሳት አንስት ለመንገር በመቃብሩ አካባቢ ተገኝተው የትንሣኤው ምስክሮች ሆነዋል፡፡
“ወእምግርማሁ ተሀውኩ ወኰኑ ከመ አብድንት እለ የአቅቡ መቃብረ “እርሱን ከመፍራት የተነሣ መቃብሩን የሚጠብቁት ታወኩ እንደ በድንም ሆኑ” ማቴ.28፥4 መልአኩም መልሶ ሴቶችን እንዲህ አላቸው “እናንተስ አትፍሩ የተሰቀለውን ኢየሱስን እንደምትሹ አውቃለሁና በዚህ የለም እርሱ እንደተናገረው ተነሥቶአል፡፡ ነገር ግን ኑና የተቀበረበትን ቦታ እዩ ፈጥናችሁም ሂዱ ከሙታን ተለይቶ ተነሣ ብሎ የትንሣኤውን የምስራች ለሴቶች መግለጡን ጽፎአል፡፡

ቅዱስ ማርቆስም በምዕራፍ 16፥1-16 ትንሣኤውን አስመልክቶ ቅዱስ ማቴዎስ የተናገረውን መሰል የትንሣኤ መልእክት ሲናገር ቅዱስ ሉቃስ በምዕራፍ 24፥1-24 ዜና ትንሣኤውን ጽፎልናል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም በወንጌል አጻጻፍ ስልቱ ከሦስቱ ወንገላውያን ረቀቅ ያለ ስልት ያለው ቢሆንም ትንሣኤው በመመስከር ከሦስት ወንጌላውያን ጋር ተባብሯል፡፡ ዮሐ.20፥1 ማርያም መግደላዊትና ሌሎች ሴቶች ወደመቃብሩ ገስግሰው በመሄድ ትንሣኤውን ለማየት እንደበቁ ለደቀ መዛሙርቱም የምሥራቹን እንደተናገሩ ዘግቦልናል፡፡ ከሦስቱ ወንጌላውያን በተለየ መልኩ ክርስቶስ ከተነሣ በኋላ በዝግ ደጅ ደቀ መዛሙርቱ ወደ አሉበት መግባቱን ትንሣኤው እንደገለጠላቸው ሰላም ለእናንተ ይሁን ብሎ የሰላም አምላክ ከሀዘናቸው እንዲጽናኑ ፍርሀታቸውን አርቆ አይዞአችሁ አትፍሩ እኔ ነኝ እጄን እግሬን እዩ በማለት ፍጹም ፍቅሩን ገልጾላቸዋል፡፡

ትንሣኤው ምትሐት አለመሆኑን ይገልጥላቸውም ዘንድ “ደቂቅየ ቦኑ ብክሙ ዘንበልዕ” ጥቂት የሚበላ አላችሁን? ብሎ ለደቀ መዛሙርቱ ተናግሯል የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ በሕቱም መቃብር መግነዝ ፍቱልኝ መቃብር ክፈቱልኝ ሳይል የተፈጸመ ኀይሉን የገለጠበት ነው ጌታ ባረገ በስምንት አመት የተጠራው ቅዱስ ጳውሎስም ትንሣኤውን ሐዋርያትን መስሎ መስክሮአል “ስለ ኃጢአታችን የተሰቀለውን ሊያስነሳንና ሊያጸድቀን የተነሣውን ጌታችንን ኢየሱስን ከሙታን ለይቶ ባስነሣው ስለምናምን ስለ እኛም ነው እንጂ” ሮሜ. 4፥25 በዚህ መልእክቱ ትንሣኤው ለእኛም ትንሣኤያችን መሆኑን ይነግረናል ትንሣኤው ለእኛ ሕይወት መሆኑንም ጭምር ሲነግረን “እርሱ ክርስቶስ በአባቱ ጌትነት ከሙታን ተለይቶ እንደተነሣ እኛም እንደ እርሱ በሐዲስ ሕይወት እንኖራለን” ሮሜ.6፥4 እንግዲህ በሞቱን ሞትን እንደሻረ በትንሣኤው ትንሣኤያችን ያበሠረ መሆኑን ደግሞም የትንሣኤያችን በኩር ጀማሪ እንደሆነ እኛ በሞቱ ብንመስለው የትንሣኤ ተካፋዮች መሆናችንን ያሳየናል፡፡

ጌታችን በአምስት ነገር በኩራችን መሆኑን መጻሕፍት ይነግሩናል
  1. በጥንት ዓለም ሳይፈጠር ዘመን ሳይቆጠር ኖሮ እኛን ፈጥሮ ለማስገኘት በኩራችን ነው፡፡
  2. በተቀድሶ/በመመስገን/ በኩራችን ነው፡፡ ቅዱሳን የጸጋ ምስጋና የሚመሰገኑት እርሱን በኩር አድርገው ነውና፡፡
  3. በትንሣኤ በኩራችን ነው፡፡ እርሱን በኩር አድርገን እንነሣለንና “አሁንም ክርስቶስ ከሞቱ ሰዎች ሁሉ አስቀድሞ ተነሥቶአል በመጀመሪያው ሰው ሞት መጥቶአል በሁለተኛው ሰው ትንሣኤ ሙታን ሆነ” 1ቆሮ.15፥20፡፡
  4. በዕርገት በኩራችን ነው፡፡ ቅዱሳን አረጉ መባሉ እርሱን በኩር አድርገው ነውና፡፡ “አርገ ከመ ያሌቡ ዕርገተ ጻድቃን ንፁሀን” የንፁሀን ጻድቃንን ዕርገት ያስረዳ ዘንድ አረገ ቅዳሴ ዩሐንስ ወልደ ነጎድጓድ”
  5. ነፍሳትን ከሲዓል አውጥቶ ምርኮን ማርኮ ገነት መንግሥተ ሰማያት በመግባት በኩራችን ነው፡፡
ስለዚህ በአለ ትንሣኤውን ስናከብር የእኛም ትንሣኤያችን መሆኑን አውቀን ተረድተን ትንሣኤ ልቡና ተነሥተን መልካም ሥራ በመሥራት መሆን አለበት እኛ ትንሣኤ ልቡና ሳንነሣ በየዓመቱ ትንሣኤን ብናከብር ፈሪሳውያንን ወይም ትንሣኤ የለም ፈርሰን በስብሰን እንቀራለን ብለው የሚያምኑ ሰዱቃውያን መምሰል ይሆናል፡፡
ትንሣኤውን ስናከብር እንዴት ማክበር እንደሚገባን ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ይላል
ከክርስቶስ ጋር ከተነሣችሁ ክርስቶስ በእግዚአብሔር ቀኛ ተቀምጦ ባለበት በላይ ያለውን እሹ የላይኛውን አስቡ በምድር ያለውንም አይደለም እናንተ ፈጽማችሁ ሞታችኋልና ሕይወታችሁም ከክርስቶስ ጋር በእግዚአብሔር ዘንድ የተሠወረች ናትና ሕይወታችሁ ክርስቶስ በሚገለጥበት ጊዜ ያን ጊዜ ከእርሱ ጋር በፍጹም ክብር ትገለጣላችሁ” ቆላ.3፥1-4 የክርስቶስ ትንሣኤ ትንሣኤያችን ነው ብለን ለምናምን ሁሉ ከምድራዊ ዐሳብ ነጻ ሆነን ተስፋ የምናደርገው ትንሣኤ እንዳለን በማሰብ ከሞት በኋላ ሕይወት ከትንሣኤም በኋላ የዘለዓለም ሞት መኖሩን ሳንዘነጋ ማክበር እንደሚገባን ይመክረናል፡፡ ላይኛውን የማያስቡ መልካም ሥራ የማይሰሩ ሰዎች ትንሣኤ ምን እንደሚመስል መድኅነ ዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ ሲያስተምር እንዲህ ብሏል፡፡ “በመቃብር ያሉ ሁሉ ቃሉን የሚሰሙበት ጊዜ ይመጣል፡፡ ስለዚህ አታድንቁ መልካም የሠሩ ለሕይወት ትንሣኤ ክፉ የሠሩም ለፍርድ ትንሣኤ ይነሣሉ” ዮሐ.5፥28 የትንሣኤያቸው በኩር ክርስቶስን አብነት አድርገው ቃሉን ሰምተው ሕጉን ጠብቀው ትዕዛዙን አክብረው ትንሣኤ ልቡና ተነሥተው የትንሣኤን ዕለት የሚያከብሩ ሥጋውን በልተው ደሙን ጠጥተው በንስሐ ተሸልመው በፍቅረ እግዚአብሔርና በፍቅረ ቢፅ /ወንድምን በመውደድ/ ጸንተው ቢኖሩ ላይኛውን ማሰብ ትንሣኤውን ማክበር ማለት ይህ ነው፡፡ የትንሣኤውን ትርጉም አውቀዋልና፡፡ ከትንሣኤ ሥጋ ትንሣኤ ልቡና ተነሥተን ሥጋውን በልተን ደሙን ጠጥተን መንግሥቱን እንድንወርስ ስሙን እንድንቀድስ እግዚአብሔር አምላካችን ይፍቀድልን፡፡
መልካም ትንሣኤ ያድርግልን አሜን፡፡