የቅዱስ ያሬድ ሥራዎችን በዩኔስኮ ማስመዝገብ እንደሚገባ ተገለጸ

የቅዱስ ያሬድ 1500ኛ ዓመት መታሰቢያ በዓልን አስመልክቶ ማኀበረ ቅዱሳን በግዮን ሆቴል ባዘጋጀውና ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን በተገኙበት አውደ ጥናት ላይ የቅዱስ ያሬድ ሕይወትና ሥራዎቹ በተባበሩት መንግሥታት የትምህርት የሳይንስና የባሕል ድርጅት /UNESCO/ ለማስመዝገብ የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ተገለጸ፡፡st yared 1500 symposium

ቅዳሜ ግንቦት 10 ሙሉ ቀን በተደረገው በዚህ ዐውደ ጥናት ላይ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የደቡባዊ ትግራይ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤ ከየአድባባራቱና ገዳማት ጥሪ የተደረገላቸው ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ምሁራን፤ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች የተገኙ ሲሆን በብፁዕነታቸው ጸሎትና ቃለምዕዳን ዐውደ ጥናቱ ተከፍቷል፡፡

ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ በሠጡት ቃለ ምዕዳን ማኅበሩ የቅዱስ ያሬድን 1500ኛ መታሰቢያ በዓልን ማዘጋጀት በመቻሉ አመስግነው በአሁኑ ወቅት በቅዱስ ያሬድ የዜማ ትምህርት ከፍተኛ እውቀት ያላቸው አባቶች ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተመናመነ መምጣቱንና በሀገረ ስብከታቸው ከሚገኙ 1000 ገዳማትና አድባራት ውስጥ በጣም ጥቂት የድጓ መምህራን ብቻ እንደሚገኙ ገልጸዋል፡፡ ይህም አሳሳቢነቱን ከፍ ስለሚያደርገው ከፍተኛ ጥረት መደረግ እንደሚገባው አሳስበዋል፡፡

በባሕልና ቱሪዝም ሚኒስቴር የሚኒስትሩ ተወካይ የሆኑት አቶ ወርቅነህ አክሊሉ ባቀረቡት ንግግር “ቅዱስ ያሬድ ወደር ያልተገኘለትና ዓለምን ያስደመመ የዜማ ጥበብ ባለቤት እንደመሆኑ የሥራ ውጤቶቹ ዘመን ተሻጋሪ ሆነው እሰካለንበት ዘመን ከነውበታቸውና ከነክብራቸው ሊደርሱ ችለዋል፡፡ ተሸናፊነትን ያሸነፈ የትእግስት ተምሳሌት በመሆን አንድን ስጋዊም ሆነ መንፈሳዊ ተግባር ከዳር ለማድረስ ያለመታከት መሥራትን በማሳየት ለተስፋ ቆራጭ ትውልድ የሕሊና ትንሳኤ አብነት ተደርጎ ሊቆጠር የሚችልና የሚገባውም ታላቅ ሊቅ ነው” በማለት ገልጸዋል፡፡

በተጨማሪም የቅዱስ ያሬድ ሥራዎች ድንበር ተሸጋሪነት ሲገልጹ “ቅዱስ ያሬድን ባሰብን ጊዜ የዘመን ውሽንፍር ያልገደባቸው ድርሰቶቹን እንደናስብ ስለሚያደርገን ዛሬም ድረስ በዚህ ሊቅ የሥራ ውጤቶች እንደ ኢትዮጵያዊነታችን እንኮራበታለን፡፡ የሌሎች ሀገሮች ህዝቦችም እንዲያውቁትና ይህ ጥበብ ድንበር ተሻጋሪ እንዲሆን ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመተባበር እንሰራለን” ብለዋል፡፡

በአውደ ጥናቱ ላይ አምስት ያህል ጥናታዊ ጽሑፎች የቀረቡ ሲሆን ከእነዚህም መካከል ሊቀ ኅሩያን በላይ መኮንን የቅዱስ ያሬድ ልደቱ፤ እድገቱ፤ የማኅሌታዊና የምናኔ ሕይወቱ በሚል ርዕስ ጥናታቸውን አቅርበዋል፡፡

ዲያቆን ሰሎሞን ወንድሙ በበኩላቸው የቅዱስ ያሬድ ዜና ሕይወቱ በተለያዩ ጸሐፍት ሥራዎች ሲዳሰስ በሚል ርዕስ ባቀረቡት ጥናትም በተለያዩ ጸሐፊያን የልደት ቀኑ፤ የእናትና አባቱ ስም፤ በስጋ ማረፉን ወይም መሰወሩን፤ የመምህራኖቹ ስም፤ . . . ወዘተ የመሳሰሉት ጉዳዮች ወጥነት ኖሯቸው መስተካከል እንደሚገባቸው መረጃ በማጣቀስ አቅርበዋል፡፡

ዲያቆን ያረጋል አበጋዝ ኦርቶዶክሳዊ ስብከት ከቅዱስ ያሬድ ድርሳናት አንጻር በተሰኘው ጥናታቸውም አንድ ኦርቶዶክሳዊ ስብከት ሊያሟላቸው ከሚገባቸው መሠረታዊ ነጥቦች አንጻር የቅዱስ ያሬድን ድርሰቶች በመመዘን አቅርበዋል፡፡

ሊቀ ጠበብት ተክሌ ሲራክ ባቀረቡት ጥናትም አራቱ የዜማ ዐበይት መንገዶች በሚል አጠር ያለ ዳሰሳ አቅርበዋል፡፡ የቤተልሔም፤ የቆሜ፤ የአጫበርና የተጉለት ዜማዎችን በትውልድ ቅብብሎሽ በመከፋፈል ለማሳየት ጥረት አድርገዋል፡፡ በተለይ የተጉለት ዜማ በመጥፋት ላይ እንደሚኝና በአሁኑ ወቅት አንድ አባት ብቻ እንደቀሩና ለትውልድ ለማሸጋገር ብዙ መሰራት እንዳለበት ጠቁመዋል፡፡

የመጨረሻው ጥናት በሙዚቃው ዘርፍ ባለሙያ የሆነውና በቅዱስ ያሬድ ሥራዎች ላይ ከፍተኛ ምርምር እያደረገ የሚገኘው ሠርፀ ፍሬ ስብሐት የቅዱስ ያሬድ ዜማ በባሕላዊውና በዘመናዊው ሙዚቃ ያለው ተጽእኖ በማስመልከት አጠር ያለ ጥናታዊ ዳሰሳ አድርገዋል፡፡

በቀረቡት አምስት ያህል ጥናቶች መነሻነት የጉባኤው ተሳታፊ በሆኑት ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን አስተያየቶችና ጥያቄዎች ተስተናግደዋል፡፡st yared 1500  2
የውይይቱ መቋጫ የሆነውም የቅዱስ ያሬድ ታሪክና ሥራዎች በተባበሩት መንግስታት የትምህርት የሳይንስና የባሕል ድርጅት /UNESCO/ ለማስመዝገብና ለዓለም ለማስተዋወቅ ጥናቶች እንዲጠኑ በማድረግና በማስተባበር አንድ እልባት ላይ መድረስ እንዲቻል ከጠቅላይ ቤተ ክህነት፤ ከሊቃውንት ጉባኤ፤ ከሊቃውንት አባቶች፤ ከባሕልና ቱሪዝም ሚኒስቴር፤ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲና ከሙዚቃ ባለሙያዎች እንዲሁም ከማኅበረ ቅዱሳን የተውጣጣ 17 አባላትን ያቀፈ ኮሚቴ እንዲዋቀር በማድረግ ዐውደ ጥናቱ ተጠናቋል፡፡

የቅዱስ ያሬድን 1500ኛ የልደት በዓል አስመልክቶ የተዘጋጀ ዐውደ ጥናት ተከፈተ

 ዲ/ን መርሻ አለኸኝ(ዶ/ር)

የቅዱስ ያሬድን 1500ኛ የልደት በዓልን ምክንያት በማድረግ በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የተዘጋጀ ዐውደ ጥናት በግዮን ሆቴል ሳባ የመሰብሰቢያ አዳራሽ ተከፈተ፡፡ በዐውደ ጥናቱ ላይ  ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ በጠቅላይ ቤተ ክህነት የልዩ ልዩ መምሪያዎች ሓላፊዎች፣ በዋና ዋና አብነት ት/ቤቶች የሚያስተምሩ መምህራንና የመንግሥትና ልዩ ልዩ ተቋማት ተወካዮችና ጥሪ የተደረገላቸው ሊቃውንት ተገኝተዋል፡፡

ቀሲስ ዶክተር ሰሙ ምትኩ የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ ባደረጉት የእንኳን ደህና መጣችሁ ንግግር ማኅበሩ ቅዱሳት መካናት ራሳቸውን ችለው የሚተዳደሩባቸውን ዘላቂ የልማት ፕሮጀክቶችን በመቅረጽና በመተግበር ለአብነት መምህራንና ተማሪዎች ድጋፍ በማድረግ ከፍተኛ ሥራ አየሠራ እንደኾነ ከገለጹ በኋላ፤ ሊቁ ለሀገራችን ከሰጠው አበርክቶ አንጻር ማኅበሩ ከፍተኛ ቦታ የሚሰጠውን የቅዱስ ያሬድን የ1500ኛ ዓመት የልደት በዓል በሰፊ ዝግጅት ለማክበር እንደወሰነ ገልጸዋል፡፡

አቶ ተስፋዬ ውብሸት የጠቅላይ ቤተ ክህነት ምክትል ዋና ሥራ አስኪያጅ ዐውደ ጥናቱን በንግግር ከፍተዋል፡፡ ምክትል ሥራ አስኪያጁ ቅዱስ ያሬድ ለሀገራችን ካበረከተው አስተዋጽዖ አንጻር የልደት በዓሉ በዚህ መልኩ መከበሩ በእጅጉ ተገቢ እንደኾነ በመጥቀስ፤ ያዘጋጀውን ማኅበረ ቅዱሳንን ካመሰገኑ በኋላ ማኅበሩ በተለይ ቅዱሳት መካናትንና አድባራትን በመርዳት በኩል እያደረገ ያለውን እንቅስቃሴ ሁሉም ኢትዮጵያዊ እንዲያግዝ ጥሪ አድርገዋል፡፡

በመቀጠልም አቶ ወርቅነህ አክሊሉ የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ሚኒስትር ተወካይ የቅዱስ ያሬድ የዜማ ሀብት ከቤተ ክርስቲያኗ አልፎ የሀገር ሀብት በመኾኑ ሁሉም እንክብካቤ እና ጥበቃ እንዲያደርግለት፣ በሕይወት ያሉትን የዜማውን ሊቃውንት ከመንከባከብ ባሻገር መዳከም የሚታይበትን የዜማውን ሽግግር ለማንቃት ተረካቢዎችን ማፍራት እንደሚገባ በመግለጽ የጉባኤውን ታዳሚ ቀልብ የገዛ ንግግር አድርገዋል፡፡

ከዐውደ ጥናቱ መርሐ ግብር ለመረዳት እንደሚቻለው በቅዱስ ያሬድ ሕይወትና ዜማዎቹ ዙሪያ በዘርፉ ሊቃውንትና ተመራማሪዎች አምስት ያህል ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበው ውይይት ይደረግባቸዋል፡፡

በተያያዘ ዜና ነገ እሑድ ግንቦት 10 ቀን 2005 ዓ፡ም ከቀኑ 7፡30 ጀምሮ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩን ጨምሮ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ ሊቃውንትና ምእመናን በተገኙበት በሰፊው እንደሚዘከር ታውቋል፡፡

ጠቅላይ ቤተ ክህነት ደብሩ በ‹‹አጥማቂው›› ላይ የጣለውን እገዳ አጸና

በምሥራቅ አዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የደብረ ሰላም ቅዱስ እስጢፋኖስ ቤተ ክርስቲያን ሰበካ ጉባኤ በቤተ ክርስቲያን ቅጽር ግቢ ‹‹ሲያጠምቅ›› በነበረው ግለሰብ ላይ ያሳለፈውን የእግድ ውሳኔ ጠቅላይ ቤተ ክህነት አጸናው፡፡ ከደብሩ ሰበካ ጉባኤ ያገኘውን የእግድ ደብዳቤ መሠረት በማድረግ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት በቁጥር 9474/756/2005 በቀን 08/09/05 ያወጣው ደብዳቤ ‹‹መ/ር ግርማ ወንድሙ ሰባኬ ወንጌልና አጥማቂ ነኝ፤ የማዳን ፈውስ አለኝ በማለት በሕገ ወጥ መንገድ እስከ አሁን ድረስ በደብሩ እያጠመቀ›› እንደሚገኝ ይገልጻል፡፡

memher girma
በማከልም ቅዱስ ሲኖዶስ በሕገ ወጥ መንገድ የማዳን ፈውስ አለኝ በማለት በየደብሩ ቅጥር ግቢ በማሰባሰብ የሚያጠምቁትን በተመለከተ ያሳለፈውን የእግድ ውሳኔ በመጥቀስ፤ ‹‹መምህር ግርማ ወንድሙ በደብረ ሰላም ቅዱስ እሰጢፋኖስ ቤተ ክርስቲያን ቅጥር ግቢ ውስጥ የሚፈጽሙት የማጥመቅ ሥርዓትና የወንጌል አገልግሎት ሕገ ወጥ መኾኑን›› በአጽንዖት በመግለጽ የደብሩ ሰበካ ጉባኤ ጽ/ቤት በግለሰቡ ላይ ያሳለፈውን ውሳኔ እንዳጸናው ይገልጻል፡፡ በተጨማሪም ከእግዱ ጋር በተያያዘ ሕዝበ ክርስቲያኑ የፀጥታ ችግር እንዳይገጥመው የደብሩ ሰበካ ጉባኤ ጽ/ቤት ጥብቅ ክትትል በማድረግ ውሳኔውን ተግባራዊ እንዲያደርግ አሳስቧል፡፡ ጠቅላይ ጽ/ቤቱ ለውሳኔው ተግባራዊነት አስፈላጊ ትብብር እንዲያደርጉ ለሚመለከታቸው የመንግሥት የፀጥታ አካላት ጥሪ አድርጓል፡፡ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ እና የደብሩ ሰበካ ጉባኤ ጽ/ቤት እግዱን ያስተላለፈበት ደብዳቤዎች የሚከተሉት ናቸው፡፡

 betekihent girma

 

 

ማእከላት ለኦዲትና ኢንስፔክሽን ሥራዎች ትኩረት እንዲሰጡ ተጠየቀ

ሚያዚያ 22 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደጀኔ

የማኅበረ ቅዱሳን ኦዲትና ኢንስፔክሽን አገልግሎት ክፍል ማእከላት ለኦዲትና ኢንስፔክሽን ሥራዎች ትኩረት እንዲሰጡ የክፍሉ ሓላፊ አቶ የሸዋስ ማሞ አስታወቁ፡፡

በአዲስ አበባ ለሁለት ቀናት ለሀገር ውስጥ ማእከላት ስለ ኦዲትና ኢንስፔክሽን አገልግሎትና አሠራር ዙሪያ ሚያዝያ 12 እና 13 ቀን 2005 ዓ.ም. በተሰጠበት ወቅት ነበር ማእከላት አገልግሎቱን አጠናክረው መቀጠል የሚገባቸው መሆኑን የተገለጸው፡፡

ማእከላት የሒሳብ ክፍል አሠራራቸውንና የኦዲትና ኢንስፔክሽን ክፍሎቻቸውን ይበልጥ  አጠናክረውና በሰው ኃይል አደራጅተው አገልግሎታቸውን መቀጠል እንዳለባቸው በሥልጠናው ላይ ተገልጿል፡፡

ለማእከላት በርካታ ሥልጠናዎችና የግንዛቤ ማስጨበጫ ዝግጅት እየተደረገ ሲሆን የማእከላቱ የግንዛቤ መጠን መጠነኛ ለውጦችን ማምጣት መቻሉን አቶ የሸዋስ ገልጸው ማእከላቱ ለኦዲትና ኢንስፔክሽን ሥራዎች ትኩረት እንዲሰጡና ክፍሉንም በባለሙያ እንዲያጠናክሩ ጥሪያቸውን ያቀረቡት፡፡ የአገልግሎት ክፍሉ እና የሒሳብ ክፍሉ መጠናከር የጎላ አስተዋጽኦ እንደሚኖረውና ለማእከላት ወጥ የሆነ የሒሳብ አያያዝ ሥርዓትም አዎንታዊ ተጽዕኖ ሊኖረው እንደሚችል አስገንዝበዋል፡፡

የአገልግሎት ክፍሉ የማኅበሩን ስልታዊ ዕቅድ ከማስፈጸም አኳያ የተለያዩ ድጋፎችን ለማእከላት የሚያደርግ መሆኑና በዕቅዱም ዘመን የራሱን የአገልግሎት ስልት ዘርግቶ እንደሚሠራ ነው ከሓላፊው ገለጻ የተረዳነው፡፡ ሚያዝያ 12 እና 13 ቀን 2005 ዓ.ም. በተሰጠው ሥልጠና በሀገር ውስጥ ከሚገኙ ማእከላት ተወካዮች በሥልጠናው መሳተፋቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡

በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚማሩ አባላት መንፈሳዋ ጉዞ አካሄዱ

ሚያዚያ 21 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዳዊት ደስ

የማኅበረ ቅዱሳን የአዲስ አበባ ማእከል “መራሔ ፍኖት” በሚል መሪ ቃል በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት እየተማሩ ላሉ የቤተ ክርስቲያን ልጆች መንፈሳዊ ጉዞ ወደ ሱሉልታ ደብረ ምሕረት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ሚያዚያ 20 ቀን 2005 ዓ.ም. አካሄደ፡፡

የጉዞውን ዓላማ አስመልክቶ አስተባባሪ የሆነው ሸዋለም ተክሉ ከዚህ ቀደም በግቢ ሲማሩ የነበሩ ተሞክሮአቸውን የሚያካፍሉበት፣ ተማሪዎች መንፈሳዊም ሆነ በሚማሩት ትምህርታቸው ያለባቸውን ጥያቄ የሚመለስበትና የክርስትና ሃይማኖት ተከታይ ሆነው ወደ ግቢ የማይመጡትን ተማሪዎችን በግቢ እየመጡ እንዲማሩ ለማድረግ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡

አያይዘውም ይህ የግቢ ጉባኤ አንድነት መርሐ ግብር ለአራተኛ ጊዜ የተካሄደ ሲሆን ከጉዞው የሚጠበቀው ውጤት በመንፈሳዊ ሕይወታቸው የዛሉ የመንፈስ ብርታት የሚያገኙበት፣ የግቢያት የአባላት ቁጥር ወደተሻለ እድገት እንዲመጣ ለማድረግ ነው ሲሉ አስተባባሪው ተናገረዋል፡፡

በዕለቱ በግቢ ጉባኤ ተማሪዎችና በዘማርያም መዝሙር ቀርቢል፣ ትምህርተ ወንጌል የተሰጠ ሲሆን ግቢያቱ በተለያየ ርዕሰ ጉዳይ የተጠየቁ ጥያቄች ምላሽ ተሰጥተውባቸዋል፡፡ በመርሐ ግብሩ ሲሳተፉ ያገኘናቸው ወጣት ዮዲት ተገኔ የሮያል ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ ተማሪ ስትሆን በዚህ ጉዞ ለመጀመሪያ ጊዜዬ ነው የተጓዝኩት፡፡ ጉዞው ትልቅ ነገር አስተምሮኛል፡፡ የሌሎችን ግቢ ጉባኤ ተማሪዎች ጋር አስተዋውቆኛል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ላይ እየተሠራ ያለውን ተግባር እንዳይ አድርጎኛል በማለት ገልጻለች፡፡

ሌላው የ5 ኪሎ ግቢ ጉባኤ ተማሪ የሆነው ናትናኤል ስዮም በጉዞው በመሳተፌ በውስጤ ይመላለስ የነበሩብኝ ጥያቄዎች ተመልሰውልኛል፡፡ እንደዚህ አይነት መርሐ ግብሮች ወጣቱን የሚያንፁ ስለሆነ ማኅበሩ አጠናክሮ ሊሠራበት የሚገባ ተግባር ነው፡፡ ሲል አስተያየቱን ሰጥቷል፡፡ በጉዞው ላይ ከ60 በላይ ከሚሆኑ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች የመጡ ከሁለት ሺህ በላይ ተጓዦች ተሳትፈዋል፡፡

ቅዱስ ፓትርያርኩ ከማኅበረ ቅዱሳን ቴሌቪዥን ጋር ልዩ ቃለ መጠይቅ አደረጉ

ሚያዚያ 17 ቀን 2005 ዓ.ም.


 abune matyas 17

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ከማኅበረ ቅዱሳን ቴሌቪዥን ጋር በዓለ ትንሣኤን ምክንያት በማድረግ ልዩ ቃለ መጠይቅ አደረጉ፡፡ በዚህ አንድ ሰዓት የፈጀ ቃለ መጠይቅ ላይ ቅዱስነታቸው ስለ ልጅነት ጊዜያቸው ፣ በትምህርት ቤት ሳሉ ስለነበሯቸው ገጠመኞች ፣ ስለ ምንኩስና ሕይወት፣ በቤተ ክርስቲያኒቱ ስላሉ ልዩ ልዩ አስተዳደራዊና ችግሮች እና በተሠጣቸው ሓላፊነት ምን ሊሠሩ እንዳሰቡ ፣ ስለ ቅድስት ሀገር የርስት ጉዳይ ከግብፅ ቤተ ክርስቲያን ጋር ለመሥራት ስለታሰበው መፍትሔ እና ስለ ዕርቀ ሰላሙ ጉዳይ ሰፋ ያለ ማብራሪያ የሠጡ ሲሆን ሙሉ ቃለ መጠይቁ በማኅበሩ የቴሌቪዥን መርሐ ግብር ከበዓለ ትንሣኤ ጀምሮ እንደሚቀርብ የማኅበሩ ሬድዮና ቴሌቪዥን ክፍል አስተባባሪ ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ ገልጸዋል፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን በኢቢኤስ ቴሌቪዥን መርሐ ግብር ከተጀመረበት የካቲት ፲፮ ፳፻፭ ጀምሮ እስከ በዓለ ትንሣኤ ድረስ ዐሥር ልዩ ልዩ መርሐ ግብራትን ያስተላለፈ ሲሆን የተጀመረበትን ሰዓት በማስተካከልም መርሐ ግብሩ ዘወትር እሑድ ከ5፡30 – 6፡00 ሰዓት ድረስ ሆኗል፡፡ የተላለፉ ዝግጅቶችም በኢንተርኔት http:// eotc.tv ላይ በማንኛውም ሰዓት መከታተል ይቻላል፡፡ ዝግጅቶቹን በመመልከት በስልክና በኢንተርኔት አድራሻዎቻችን ገንቢ አስተያየቶቻችሁን የሠጣችሁን ምዕመናንን እያመሰገንን ለበለጠ ሥራ ረድኤተ እግዚአብሔር እንዳይለየን ጸልዩልን ሲሉ የክፍሉ አስተባባሪ ገልጸዋል፡፡  

ሠራተኛ ጉባኤያት በቤተ ክርስቲያን ትልቅ ድርሻ እንደሚጠበቅባቸው ተገለጸ

ሚያዚያ 15 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዳዊት ደስታ

sera 2 1የማኅበረ ቅዱሳን የአዲስ አበባ ማእከል ትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ክፍል የሠራተኛ ጉባኤ የአንድነት መርሐ ግብር ሚያዚያ 13 ቀን 2005 ዓ.ም. በጠቅላይ ቤተ ክህነት የስብከተ ወንጌል አዳራሽ በተካሄደው መርሐ ግብር ሠራተኛ ጉባኤያት በቤተ ክርስቲያን ትልቅ ድርሻ እንደሚጠበቅባቸው ተገለጸ፡፡

የመርሐ ግብሩን ዓላማ አስመልክቶ የትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ክፍል ሓላፊ የሆኑት ኀይለ ማርያም መድኅን “በአዲስ አበባ ማእከል ሥር ሆነው የሚማሩ 22 የሚደርሱ የሠራተኛ ጉባኤያት ለቤተ ክርስቲያን እውቀታቸውን፣ ገንዘባቸውን፣ ጊዜያቸውን ሊያበረክቱ የሚያስችላቸውን ነገር ማስጨበጥና በተደራጀ ሁኔታ ቤተ ክርስቲያንን በአቅም ማገልገል የሚችሉበትን ሁኔታ ለመፍጠር ነው” በማለት ገልጸዋል፡፡

አያይዘውም እንደዚህ ዓይነት መርሐ ግብር ሲዘጋጅ የመጀመሪያ ጊዜ በመሆኑ ወደፊት የተለያዩ የሠራተኛ ጉባኤያትን በአንድነት ለማጠናከር በቤተ ክርስቲያን ከዚህ ቀደም ከሚሠሩት የተሻለ ሥራ እንዲሠሩ ለማድረግ የታሰበ ነው በማለት ሓላፊው ተናግረዋል፡፡

በዕለቱ በዲ/ን ያረጋል አበጋዝ “የቤተ ክርስቲያን ተልዕኮና ዓላማ እና የልጆቿ ድርሻ” በሚል ጥናታዊ ጽሑፍ፣ ትምህርተ ወንጌልና መዝሙር ቀርቧል፡፡ በቀረበው ጥናታዊ ጽሑፍsera 2 2 አስተያየትና ጥያቄዎች ቀርበው ከጥናት አቅራቢው ምላሽ ተሰጥቶባቸዋል፡፡

በመርሐ ግብሩ ላይ ሲሳተፉ ያገኘናቸው አቶ ተስፋዬ አሻግሬ “በዛሬዋ ቀን በመገኘቴ ትልቅ ደስታ ተሰምቶኛል፡፡ ምክንያቱም በርካታ መሥሪያ ቤቶች ጉባኤ ያካሂዳሉ፡፡ ከመማር ባለፈ ምንም ድርሻ እንዳለን እንኳ አናውቅም ነበር፡፡ ዛሬ ግን ቤተ ክርስቲያናችን ከኛ ከልጆቿ ብዙ ነገር እንደምትጠብቅና መሥራት እንደምንችል አውቄበታለው” በማለት ገልጸዋል፡፡

በዕለቱ በተደረገው መርሐ ግብር ከአምስት መቶ በላይ የሆኑ በተለያየ መሥሪያ ቤት የሚሠሩ የሠራተኛ ጉባኤ ተሳታፊዎች ተገኝተዋል፡፡

ለአብነት ተማሪዎች በጤና አጠባበቅ ላይ ያተኮረ ሥልጠና ተሰጠ

ሚያዚያ 14 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

healthበማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ከጎንደር ማእከል ጋር በመተባበር በጎንደር ውስጥ ከሚገኙ አብነት ትምህርት ቤቶች ለተውጣጡ ተማሪዎች በግልና በአካባቢ ንጽህና አጠባበቅ ላይ ያተኮረና አንድ ቀን የወሰደ ስልጠና በደብረ ኀይል ወደብረ ጥበብ በዓት ለማርያም ቤተ ክርስቲያን አዳራሽ  ሚያዚያ 12 ቀን 2005 ዓ.ም. ተሰጠ፡፡

“ጤና ሀብት ነው” በሚል መሪ ቃል የተሰጠውን ሥልጠና በማስመልከት በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የአብነት ትምህርት ቤቶች ክትትል ክፍል ምክትል ኃላፊና የፕሮጀክቱ አስተባባሪ ሊቀ ዲያቆን መሐሪ መዘምር የሥልጠናውን ዓላማ አስመልክቶ በሰጡት ማብራሪያ “በአብነት ትምህርት ቤቶች ውስጥ ከፍተኛ የሆነ የጤና ችግሮች ይታያሉ፡፡ ይህንንም መነሻ በማድረግ 25 ሺህ ተማሪዎችን ተጠቃሚ የሚያደርግ ፕሮጀክት በመቅረጽ የጤና አጠባበቅ ትምህርት ለአብነት ትምህርት ተማሪዎች ለመስጠት አቅደን ወደ ትግበራ በመሸጋገር ላይ እንገኛለን፡፡ ጎንደር ከተማ ውስጥ እስከ 2000 ተማሪዎች ይገኛሉ ተብሎ ስለሚገመት ለሁሉም ሥልጠና ለመስጠት ስለሚያዳግት ከየአብነት ትምህርት ቤቱ ለተውጣጡ 200 ተማሪዎች ሥልጠናውን እየሰጠን እንገኛለን፡፡ ተማሪዎቹም በአብነት ትምህርት ቤቶቻቸው ውስጥ ለሚገኙ ጓደኞቻቸው የአቻ ለአቻ ሥልጠና እንዲሰጡ እናደርጋለን፡፡” ብለዋል፡፡

በጎንደር ማኅበረ ቅዱሳን ማእከል የአብነት ትምህርት ቤቶቹን የጤና አጠባበቅ ሁኔታ የሚከታተልና የሚቆጣጠር ኮሚቴ እንደሚዋቀር የተገለጸ ሲሆን የግልና የአካባቢ ንጽህና ለመጠበቅ የሚረዱ ቁሳቁሶች እደላና አጠቃሙን ለማሳየት በየአብነት ትምህርት ቤቶቹ የሙከራ ሥራ እንደሚሠራ ሊቀ ዲያቆን መሐሪ መዘምር ገልጸዋል፡፡

ከመንበረ ፀሐይ ቁስቋም ማርያም ገዳም የቅኔ ጉባኤ ቤት ተማሪ የሆኑት መሪ ጌታ ዮሴፍ ታረቀኝ ስለ ሥልጠናው ጠቀሜታ ሲገልጹ “አብሮ ስላደገብን ቀሸሽ ብለን ስለምንታይ ለተለያዩ በሽታዎች ስንጋለጥ ኖረናል፡፡ ንጽሕናችንን መጠበቅ የሚጠቅመው ራሳችንን ስለሆነ ማኅበረ ቅዱሳን እየሰጠን ያለውን ስልጠና ወስጄ ለተማሪዎች በቅኔ ነገራ ወቅትም ሆነ አመቺ በሆነ ስዓት ለማስተማር ተዘጋጅቻለሁ” ብለዋል፡፡

ስልጠናው የግልና የአካባቢ ንጽሕና አጠባበቅ፤ የውኃ አያያዝና አጠቃቀም፤ የምግብ አያዝና አጠቃቀም፤ የበሽታ መንስኤዎች፤ የበሽታ መተላለፊያ መንገዶች፤ ተላላፊ በሽታዎችን መከላከል፤ ወባ፤ የግርሻ በሽታ፤ . . . የሚሉ ርዕሶችን ያካተተ ሲሆን ለሃያ አምስት ሺህ ተማሪዎች በአራት ዓመታት ውስጥ ተጠቃሚ ለማድረግ እስከ አንድ ሚሊዮን ብር እንደሚፈጅ ተገልጧል፡፡  

ኒቆዲሞስ

ሚያዚያ 12 ቀን 2005 ዓ.ም.

በመ/ር ሳሙኤል ተስፋዬ

እግዚአብሔር “ጾምን ቀድሱ ጉባኤውንም ዐውጁ ሽማግሌዎችንና በምድር የሚኖሩትን ሁሉ ወደ አምላካችሁ ወደ እግዚአብሔር ሰብስቡ ወደ እግዚአብሔርም ጩኹ በጽዮን መለከት ንፉ ጾምንም ቀድሱ” በማለት ዐውጀን መጾም ያለብንን ጾም እንድንፆም በነብዩ ኢዩኤል ነግሮናል፡፡ ኢዩ.1፥14፣ 2፥15

እግዚአብሔር ሙሴን በእሥራኤል ልጆች ዘንድ ከሰውም ከእንስሳም ማኅፀንን የሚከፍት በኲርን ሁሉ ለእኔ ቀድስልኝ በማለቱ /ዘጸ.13፥12 ከሰው፣ ከዕለታትት ተለይተው የተቀደሱ ነበሩ፡፡ አጽዋማትም በዐዋጅ ተለይተው ይጾማሉ፡፡ ከእነዚህ ውስጥም፡- የዐብይ ጾም ይገኛል፡፡

ዐብይ ጾም ዐብይነቱ ነብያት፣ ሐዋርያት፣ ቅዱሳን የጾሙት ጾም ሳይሆን የጠፋውን የሰውን ልጅ ለመፈለግ፣ የሞተውን አዳምን ለማስነሣት አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው ሆኖ ወደዚህ ዓለም የመጣው ወልደ አብ ወልደ ማርያም በመብል የተጀመረውን የሞት መንገድ ለማጥፋት በጾም ስለጀመረው ነው፡፡

አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመዋዕለ ሥጋዌው ያደረጋቸውን የድኅነት ጉዞና ድንቅ ድንቅ ተአምራት ዋጋ የተከፈለባቸው በመሆናቸው አባቶቻችን በሠሩልን ሥርዓት መሰረት በዐብይ ጾም ወራት ዘወረደ ብለን ጀምረን ትንሣኤ ብለን አስከምናከብርበት ድረስ ያሉትን ሰንበታት ለሰው ልጆች የተከፈለልንን ዋጋ እያሰብን እንማረዋለን፣ አንዘምራለን፣ እንጸልያለን፡፡ ከነዚህ ሰንበታት በ7ኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው ደግሞ ኒቆዲሞስ ተብሎ ተሰይሞ ይከበራል፡፡

ከፈሪሳውያን ወገን የአይሁድ አለቃ በነበረው በኒቆዲሞስ የተሰየመ ሰንበት ነው፡፡ የአይሁድ አለቆች አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስን “ምልክት አሳየን” እያሉ ይፈታተኑት ነበር፡፡ ስለሞቱና ትንሣኤው በምሳሌ ቢነግራቸው አልገባቸውም፡፡ ሲያስተምር ብዙዎች ያምኑ ነበር፡፡ ለአይሁድ አለቆች ግን ጭንቅ ነበር፤ የታመሙ ሲፈወሱ ሕጋችን ተሻረ ይሉ ነበር፡፡ በዚህ ሁሉ ተአምራትና ትምህርት የአይሁድ አለቆች ክርስቶስን ለመክሰስ በሚፈልጉበት ወቅት ከአይሁድ አለቆች አንዱ ኒቆዲሞስ በቀን እንዳያደርገው አይሁድን ፈርቶ አንድም ጊዜ አላደርሰው ብሎ እንደ አይሁድ አለቆች ኢየሱስን መቃወሙን ትቶ በሌሊት ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘንድ ሄደ፡፡

አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በነፍስ የታመሙትን በቃሉ በሥጋ የታመሙትን በተአምራቱ ሲፈውስ፤ ኒቆዲሞስ ሰምቶና ተመልክቶ “መምህር ነኝ” ብሎ በመምህርነቱ ሳይኮራ አለቅነቱን መመኪያ ሳያደርግ፡፡ በልቦናው የተሳለውን እውነትን የመፈለግ ስሜት አንግቦ ጌታው መምህሩ ዘንድ በሌሊት ገሠገሠ ዮሐ.3÷1

ደርሶም ምስክርነቱን እንዲህ ሲል መስጠት ጀመረ “መምህር ልታስተምር ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደመጣህ እናውቃለን፡፡ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ከሆነ በቀር አንተ የምታደርገውን ተአምራት ሊያደርግ የሚችል የለምና” ዮሐ.9÷24፣ የሐዋ.ሥራ 10÷38 በማለት መመስከር ሲጀምር ጎዶሎን የሚሞላ፡፡ አላዋቂነት በአዋቂነት የሚለውጥ፡፡ ከምድራዊ እውቀት ወደ ሰማያዊ ምስጢር የሚያሸጋግር አምላክ፡፡ “ዳግመኛ ያልተወለደ የእግዚአብሔርን መንግሥት ለማየት አይችልም” ዮሐ.3÷6 1ጴጥ.1÷23 በማለት የአይሁድ መምህር ለሆነው ኒቆዲሞስ ቢያስተምረው ስለዳግመኛ መወለድ ከመጽሐፍ ቢያገኘውም ምስጢሩ አልተገለጠለትምና “ሰው ከሸመገለ በኋላ ዳግመኛ መወለድ እንደምን ይቻላል? ዳግመኛ ይወለድ ዘንድ ወደ እናቱ ማኅፀን ተመልሶ መግባት ይችላልን?” በማለት ጥያቄ አቅርቧል፡፡

“እውነት እውነት እልሃለሁ ዳግመኛ ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ ያልተወለደ ወደ እግዝአበሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም፡፡ ኤፌ.5÷26 ከሥጋ የተወለደ ሥጋ ነው፡፡ ከመንፈስም የተወለደ መንፈስ ነውና፡፡ በማለት አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቢያስረዳው ምስጢሩ ከአቅሙ በላይ የሆነበት ኒቆዲሞስ እንደምን ይቻላል? በማለት ጠይቋል፡፡ አበ ብዙኀን አብርሃም ከአምላኩ ሞገስን አግኝቶ፤  የሰዶምና ገሞራ ጥፋት እንዳይደርስ እያማለደ ከእግዚአብሔር ጋር ሲነጋገር እንደ ነበረ፤ ኒቆዲሞስም አላዋቂነቱን አምኖ ያልገባውን ምስጢር አምላኩን የመጠየቅ ዕድል በማግኘቱ ሲጠይቅ፣ ኢየሱስ ክርስቶስም “አንተ የእስራኤል መምህራቸው ነህ ግን ይህን ነገር አታውቅምን? በምድር ያለውን ስንነግራቸው ካላመናችሁ በሰማይ ያለውን ብንነግራችሁ እንደምን ታምናላችሁ? ከሰማይ ከወረደው ከሰው ልጅ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ የለም ….፡፡ሙሴ ምድረ በዳ እባቡን እንደ ሰቀለ የሰው ልጅ እንዲሁ ይሰቀላል፡፡ ያመኑበት ሁሉ ለዘለዓለም ሕያው ሆኖ እንዲኖር እንጂ እንዲጠፉ አይደለም…..” ዮሐ.3÷14፡፡ እያለ ለድኅነተ ዓለም እንደ መጣ ሰው በመብል፣ አምላኩን ከድቶ ልጅነቱን ትቶ ከእግዚአብሔር ቢለይም የሰው ልጅ ያጣውን ልጅነት ለመመለስ ስመ ግብርና ሀብተ ወልድን ለመስጠት መምጣቱን አስረዳው፡፡ “ሐወጽከኒ ሌሊተ ወፈተንኮ ለልብየ፡፡ አመከርከኒ ወኢተረከ በዓመፃ በላዕሌየ፡፡ ከመ ኢይንብብ አፉየ ግብረ እጓለ እመሕያው፡፡ ልቤን ፈተንከው በሌሊትም ጎበኘኸኝ ፈተንከኝም ምንም አላገኘህብኝም፡፡ የሰውን ሥራ አፌ እንዳይናገር ፈቃዴ ነው” መዝ.16÷3 እንዳለ ቅዱስ ዳዊት ምስጢረ ሥጋዌን የድኅነት ምስጢር ገልጾለታል፡፡

በሌሊት ከአምላኩ ተምሮ ምስጢሩ የተገለጸለት ኒቆዲሞስ ፍርሃት ርቆለት ቀድሞ በአደባባይ ሄዶ መማርን የፈራ ምስጢሩ ሲገለጽለት አይሁድ በሰቀሉት ዕለት ሳይፈራ ከአርማትያሱ ዮሴፍ ጋር ቅዱስ ሥጋውን ገንዞ ለመቅበር በቃ “ወአልቦ ፍርሃት ውስተ ተፋቅሮትነ፡፡ ፍጹም ፍቅር ፍርሃትን አውጥቶ ይጥላል ማቴ.27÷58፣ 1ዮሐ.4÷18 እንዲል፡፡

ያመነ የተጠመቀ ይድናል፡፡ ያላመነ ያልተጠመቀ ይፈረድበታል ማር.16÷16፡፡ ባለው አማናዊ ቃል ኪዳን መሠረት አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስን እንደ አምላክነቱ አምነን  ለመንግሥቱ ዜጋ እንድንሆን ለኒቆዲሞስ ምስጢሩን ጥበቡን የገለጸ አምላክ ለኛም ይግለጽልን፡፡