merahi mk exhibition1

መራሒ

merahi mk exhibition1

የትንሣኤ የቅዳሴ ምንባብ 1 (1ቆሮ. 15፥20-41)

አሁንም ክርስቶስ ከሞቱ ሰዎች ሁሉ አስቀድሞ ተነሥቶአል፡፡ በመጀመሪያው ሰው ሞት መጥቶአልና፥ በሁለተኛው ሰው ትንሳኤ ሙታን ሆነ፡፡ ሁሉ በአዳም እንደሚሞት እንዲሁ በክርስቶስ ሁሉ ሕያዋን ይሆናሉ፡፡ ነገር ግን ሰው ሁሉ በየሥርዐቱ ይነሣል፤ በመጀመሪያ ከሙታን የተነሣ ክርስቶስ ነው፤ ከዚያ በኋላ በክርስቶስ ያመኑ እርሱ በሚመጣበት ጊዜ ይነሣሉ፡፡ እግዚአብሔር አብ መንግሥቱን እጅ ባደረገ ጊዜ፥ ገዥም ሁሉ፥ ንጉሥም ሁሉ፥ ኀይልም ሁሉ በተሻረ ጊዜ፥ያን ጊዜ ፍጻሜ ይሆናል፡፡ ጠላቶቹ ሁሉ ከእግሩ በታች እስኪወድቁ ድረስ ይነግሥ ዘንድ አለውና፡፡ ከዚያ በኋላ የመጨረሻው ጠላት ይሻራል፤ ይኸውም ሞት ነው፡፡ ሁሉን ከእግሩ በታች አስገዝቶለታልና፥ “ሁሉ ይገዛለት” ባለ ጊዜ ግን ሁሉን ከሚያስገዛለት በቀር እንደ ሆነ የታወቀ ነው፡፡ ሁሉም በተገዛለት ጊዜ ግን እግዚአብሔር በሁሉ ቦታ በሁሉ ይሆን ዘንድ፥ ያን ዕለት ወልድም ሁሉን ላስገዛለት ይገዛል፡፡
ያለዚያማ ለምን ያጠምቃሉ? ሙታን እንዲነሡ አይደለምን? እንግዲህ እኛስ ሁልጊዜ መከራን ስለምን እንቀበላለን? ወንድሞቻችን ሆይ፥ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ በሆነውና በእናንተ ላይ ባለኝ ትምክህት ሁል ጊዜ እገደላለሁ፡፡ በውኑ በኤፌሶን ከአውሬ ጋር የታገልሁ ለሰው ብዬ ነውን? ምንስ ይጠቅመኛል? ሙታን የማይነሡ ከሆነ እንግዲህ እንብላ እንጠጣ፥ ነገም እንሞታለን፡፡ ወንድሞቻችን አያስቱአችሁ፤ ክፉ ነገር መልካም ጠባይን ያበላሻልና፡፡
ለጽድቅ ትጉ፤ አትሳቱ፤ እግዚአብሔርን የማያውቁት ሰዎች አሉና፤ ነገር ግን እንድታፍሩ ይህን እላችኋለሁ፤ ሙታን እንዴት ይነሣሉ? የሚነሡስ በምን አካላቸው ነው? የሚል አለ፡፡ አንተ ሰነፍ! አንተ የምትዘራው እንኳን ካልፈረሰ አይበቅልም፡፡ የምትዘራውም የስንዴ ቢሆን፥ የሌላም ቢሆን የምትዘራት ቅንጣት ብቻ ናት እንጂ ይህ ኋላ የሚገኘው አገዳው አይደለም፡፡ እግዚአብሔር ግን እንደ ወደደ አገዳን ይሰጠዋል፤ ለእያንዳንዱ ዘርም አገዳው እየራሱ ነው፡፡ የፍጥረቱ ሁሉ አካል አንድ አይደለምና፤ የሰው አካል ሌላ ነው፤ የእንስሳም አካል ሌላ ነው፤ የወፍ አካልም ሌላ ነው፤ የዓሣ አካልም ሌላ ነው፡፡ ሰማያዊ አካል አለ፤ ምድራዊ አካልም አለ፤ ነገር ግን በሰማይ ያለው አካል ክብሩ ልዩ ነው፤ በምድርም ያለው አካል ክብሩ ልዩ ነው፤ የፀሐይ ክብሩ ሌላ ነው፤ የጨረቃም ክብሩ ሌላ ነው፤ የከዋክብትም ክብራቸው ሌላ ነው፤ ኮከብ ከኮከብ በክብር ይበልጣልና፡፡

የትንሣኤ የቅዳሴ ምንባብ 2( 1ጴጥ.1፥1-13)

ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ ከጴጥሮስ፥ በጳንጦስ፥ በገላትያና በቀጰዶቅያ፥ በእስያና በቢታንያ ሀገሮች ለተበተኑ ስደተኞች፥ እግዚአብሔር አስቀድሞ እንዳወቃቸው፥ በመንፈስ ቅዱስም እንደሚቀደሱ፥ ይታዘዙና በኢየሱስ ክርስቶስ ደም ይረጩ ዘንድ፥ ለተመረጡት፥ ጸጋና ሰላም ይብዛላችሁ፡፡
ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን በመነሣቱ፥ ለሕያው ተስፋ እንደ ምሕረቱ ብዛት ሁለተኛ የወለደን የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አባት እግዚአብሔር ይመስገን፡፡ የማያረጀውን፥ የማይለወጠውንና የማይጠፋውን፥ በሰማያት ለእኛና ለእናንተ ተጠብቆልን ያለውን ለመውረስ፥ በኋላ ዘመን በሃይማኖት ትገለጥ ዘንድ ለተዘጋጀችው ድኅነት በእግዚአብሔር ኀይል ለተጠበቃችሁት፥ እስከ ዘለዓለም ደስ ይላችኋል፤ ነገር ግን በሚመጣባችሁ ልዩ ልዩ መከራ አሁን ጥቂት ታዝናላችሁ፡፡ በእሳት ከአጠሩት ከጥሩ ወርቅ በሚመረጥ ሃይማኖታችሁ እንደምትቀበሉት መከራ መጠን ኢየሱስ ክርስቶስ በሚገለጥበት ጊዜ በክብር፥ በጌትነትና በምስጋና ትገኛላችሁ፡፡ እርሱም ሳታዩት የምትወዱት ነው፤ እስከ ዛሬም ድረስ አላያችሁትም፤ ነገር ግን ታምኑበታላችሁ፤ አሁንም ፍጻሜ በሌላትና በከበረች ደስታ ደስ ይላችኋል፡፡ በሃይማኖታችሁም ፍጹምነት የነፍሳችሁን ድኅነት ታገኛላችሁ፡፡
ለእናንተም ስለሚሰጠው ጸጋ ትንቢት የተናገሩ ነቢያት የመረመሩአትና የፈለጉአት መድኀኒት ናት፡፡ በእነርሱም የነበረ የክርስቶስ መንፈስ ስለ ክርስቶስ መከራ፥ ከእርሱም በኋላ ስለሚመጣው ክብር፥ አስቀድሞ እየመሰከረ በምን ወይም እንዴት ባለ ዘመን እንዳመለከተ ይመረምሩ ነበር፡፡ ለእነርሱም ከሰማይ በተላከ በመንፈስ ቅዱስ ወንጌልን የሰበኩላችሁ ሰዎች አሁን በነገሩአችሁ ነገር እናንተን እንጂ ራሳቸውን እንዳላገለገሉ ተገለጠላቸው፡፡ ይህንም ነገር መላእክቱ ሊመለከቱ ይመኛሉ፡፡ ስለዚህ የልቡናችሁን ወገብ ታጥቃችሁና ነቅታችሁ ኑሩ፤ ኢየሱስ ክርስቶስም ሲገለጥ የምታገኙትን ጸጋ ፈጽማችሁ ተስፋ አድርጉ፡፡

የትንሣኤ የቅዳሴ ምንባብ 3( ሐዋ.2፥22-37)

“እናንተ የእስራኤል ሰዎች ሆይ፥ ይህን ነገር ስሙ፤ እንደምታውቁት በመካከላችሁ እግዚአብሔር በእጁ ባደረገው በከሃሊነቱ በተአምራቱና በድንቅ ሥራዎቹ እግዚአብሔር የገለጠላችሁን ሰው የናዝሬቱን ኢየሱስን ስሙ፡፡ እርሱንም በተወሰነው በእግዚአብሔር ምክርና በቀደመው ዕውቀቱ እናንተ አሳልፋችሁ በኃጥኣን እጅ ሰጣችሁት፤ ሰቅላችሁም ገደላችሁት፡፡ እግዚአብሔር ግን የሞትን ማሰሪያ ፈቶ ከሙታን ለይቶ አስነሣው፤ ሞት እርሱን ሊይዘው አይችልምና፡፡ ዳዊትም ስለ እርሱ እንዲህ አለ፡- እግዚአብሔርን ሁል ጊዜ በፊቴ አየዋለሁ፤ እንዳልታወክ በቀኜ ነውና፡፡ ስለዚህ ልቤን ደስ አለው፤ አንደበቴም ሐሤት አደረገ፤ ሥጋዬም ደግሞ በተስፋው አደረ፡፡ ነፍሴን በሲኦል አትተዋትምና፥ ጻድቅህንም ጥፋትን ያይ ዘንድ አትሰጠውምና፡፡ የሕይወትን መንገድ አሳየኸኝ፤ ከፊትህ ጋራ ደስታን አጠገብኸኝ፡፡
“እናንተ ወንድሞች ሆይ፥ ስለ አባቶች አለቃ ስለ ዳዊት ነገር እንደ ሞተ እንደ ተቀበረም፥ መቃብሩም እስከ ዛሬ ድረስ በእኛ ዘንድ እንደ አለ ገልጬ እንድነግራችሁ ትፈቅዱልኛላችሁን? ነቢይ ስለ ነበረ፥ ከአብራኩም የተገኘውን በዙፋኑ እንዲያነግሥለት እግዚአብሔር መሐላን እንደ ማለለት ስለ ዐወቀ፥ ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ እንደሚነሣ፥ ሥጋዉም በመቃብር እንደማይቀር፥ ጥፋትንም እንደማያይ አስቀድሞ ዐውቆ ተናገረ፡፡ እርሱን ኢየሱስን እግዚአብሔር አስነሣው፤ ለዚህም እንደማያይ አስቀድሞ ዐውቆ ተናገረ፡፡ እርሱን ኢየሱስን እግዚአብሔር አስነሣው፤ ለዚህም እኛ ሁላችን ምስክሮቹ ነን፡፡ አሁን ግን በእግዚአብሔር ቀኝ ከፍ ከፍ ብሎና የመንፈስ ቅዱስን ተስፋ ከአብ ገንዘብ አድርጎ ይህን ዛሬ የምታዩትንና የምትሰሙትን አፈሰሰው፡፡ ዳዊት ወደ ሰማይ አልወጣም፥ ነገር ግን እርሱ አለ፡- ጌታ ጌታዬን አለው፡- በቀኜ ተቀመጥ፡፡ ጠላቶችህን ከእግርህ ጫማ በታች እስክጥላቸው ድረስ፡፡ እንግዲህ የእስራኤል ወገኖች ሁሉ እናንተ የሰቀላችሁትን ኢየሱስን እግዚአብሔር ጌታም መሢሕም እንዳደረገው በርግጥ ይወቁ፡፡” ይህንም በሰሙ ጊዜ ልባቸው ተከፈተ፤ ጴጥሮስንና ወንድሞቹ ሐዋርያትንም፥ “ወንድሞቻችን ሆይ፥ ምን እናድርግ?” አሏቸው፡፡

የትንሣኤ የቅዳሴ ምንባብ 4( ዮሐ.20፥1-19)

ከሳምንቱም በመጀመሪያዉ ቀን ማርያም መግደላዊት በማለዳ ገና ጨለማ ሳለ ወደ መቃብር መጣች፤ ድንጋዩንም ከመቃብሩ አፍ ተነሥቶ አገኘችው፡፡ ፈጥናም ወደ ስምዖን ጴጥሮስና ጌታችን ኢየሱስ ይወደው ወደ ነበረው ወደዚያ ወደ ሌላዉ ደቀ መዝሙር መጥታ፥ “ጌታዬን ከመቃብር ወስደውታል፤ ወዴትም እንደ ወሰዱት አላውቅም” አለቻቸው፡፡ ጴጥሮስና ያ ሌላዉ ደቀ መዝሙርም ወጥተው ወደ መቃብሩ ሄዱ፡፡ ሁለቱም በአንድነት ሲሮጡ ያ ሌላዉ ደቀ መዝሙር ጴጥሮስን ቀድሞት ወደ መቃብሩ ደረሰ፡፡ ጐንበስ ብሎም ሲመለከት በፍታዉን ተቀምጦ አየ፤ ነገር ግን ወደ ውስጥ አልገባም፡፡ ስምዖን ጴጥሮስም ተከትሎት ደረሰና ወደ መቃብሩ ገባ፤ በፍታዉንም በአንድ ወገን ተቀምጦ አየ፤ በራሱ ላይ የነበረው መጠምጠሚያም ሳይቃወስ ለብቻው ተጠቅልሎ አየ፤ ከበፍታዉ ጋርም አልነበረም፡፡ ከዚህም በኋላ አስቀድሞ ወደ መቃብሩ የደረሰው ሌላዉ ደቀ መዝሙር ገባ፤ አይቶም አመነ፤ ከሙታን ተለይቶ ይነሣ ዘንድ እንደ አለው በመጻሕፍት የተጻፈውን ገና አላወቁም ነበርና፡፡ ከዚህም በኋላ ደቀ መዛሙርቱ ተመልሰው ወደ ቤታቸው ገቡ፡፡
ማርያም ግን ከመቃብሩ በስተውጭ እያለቀሰች ቆማ ነበረ፤ እያለቀሰችም ወደ መቃብሩ ጐንበስ ብላ ተመለከተች፡፡ ሁለት መላእክትንም ነጭ ልብስ ለብሰው የጌታችን የኢየሱስ ሥጋ በነበረበት ቦታ አንዱ በራስጌ፥ አንዱም በግርጌ ተቀምጠው አየች፡፡ እነዚያ መላእክትም፥ “አንቺ ሴት፥ ምን ያስለቅስሻል?” አሉአት፤ እርስዋም፥ “ጌታዬን ከመቃብር ውስጥ ወስደውታል፤ ወዴትም እንደ ወሰዱት አላውቅም” አለቻቸው፡፡ ይህንም ተናግራ ወደ ኋላዋ መለስ ስትል ጌታችን ኢየሱስን ቆሞ አየችው፤ ጌታችን ኢየሱስም እንደ ሆነ አላወቀችም፡፡ ጌታችን ኢየሱስም፥ “አንቺ ሴት፥ ምን ያስለቅስሻል? ማንንስ  ትሺያለሽ?” አላት፤ እርስዋ ግን የአትክልት ቦታ ጠባቂ መስሎአት፥ “ጌታዬ፥ አንተ ወስደኸው እንደ ሆነ ሄጄ ወደ እኔ እንዳመጣውና ሽቱ እንድቀባው ወዴት እንደ አኖርኸው ንገረኝ” አለችው፡፡ ጌታችን ኢየሱስም፥ “ማርያም!” አላት፤ እርስዋም መለስ ብላ በዕብራይስጥ ቋንቋ፥ “ረቡኒ!” አለችው፤ ትርጓሜዉም “መምህር” ማለት ነው፡፡ ጌታችን ኢየሱስም፥ “አትንኪኝ፤ ገና ወደ አባቴ አላረግሁምና፤ ነገር ግን ወደ ወንድሞቼ ሂጂና፡- ወደ አባቴ፥ ወደ አባታችሁ ወደ አምላኬ፥ ወደ አምላካችሁ አርጋለሁ አለ ብለሽ ንገሪአቸው” አላት፡፡ ማርያም መግደላዊትም ሄደች፤ ጌታን እንደ አየች፥ ይህንም እንዳላት ለደቀ መዛሙርቱ ነገረቻቸው፡፡
ያም ከሳምንቱ የመጀመሪያው ቀን በመሸ ጊዜ ደቀ መዛሙርቱ አይሁድን ስለ ፈሩ ተሰብስበው የነበሩበት ቤት ደጁ ተቈልፎ ሳለ ጌታችን ኢየሱስ መጥቶ በመካከላቸው ቆመና፥ “ሰላም ለእናንተ ይሁን” አላቸው፡፡

የትንሣኤ የማሕሌት ምንባብ 3 (ሉቃ.24፥1-13)

ከሳምንቱም በመጀመሪያዪቱ ቀን ያዘጋጁትን ሽቶ ይዘው እጅግ ማልደው ወደ መቃብሩ ሄዱ፤ ሌሎች ሴቶችም አብረዋቸው ነበሩ፡፡ ያቺንም ድንጋይ ከመቃብሩ ላይ ተንከባልላ አገኙአት፡፡ ገብተውም የጌታችን የኢየሱስን ሥጋ አላገኙም ስለዚህም ነገር የሚሉትን አጥተው ሲያደንቁ ሁለት ሰዎች ከፊታቸው ቆመው ታዩአቸው፤ ልብሳቸውም ያብረቀርቅ ነበር፡፡ ፈርተውም ፊታቸውን ወደ ምድር አቀረቀሩ፡፡ እነርሱም እንዲህ አሉአቸው፥ “ሕያዉን ከሙታን ጋር ለምን ትሹታላችሁ? በዚህ የለም፤ ተነሥቶአል፡፡ በገሊላ ሳለ ለእናንተ እንዲህ ሲል የተናገረውን ዐስቡ፡- የሰው ልጅ በኀጢአተኞች ሰዎች እጅ ተላልፎ ይሰጥ ዘንድ አለው፤ ይሰቅሉታል፤ ይገድሉታል፤ በሦስተኛውም ቀን ይነሣል፡፡” ቃሉንም ዐስቡ፡፡ ከመቃብርም ተመልሰው ለዐሥራ አንዱና ለቀሩት ባልጀሮቻቸውም ይህን ለሐዋርያት ነገሩአቸው፡፡ ይህም ነገር በፊታቸው እንደ ተረት መሰላቸውና አላመኑአቸውም፡፡ ጴጥሮስም ተነሣ፤ ወደ መቃብርም ፈጥኖ ሄደ፤ ዝቅ ብሎም በተመለከተ ጊዜ በፍታውን ለብቻው ተቀምጦ አየ፤ የሆነውንም እያደነቀ ተመለሰ፡፡
በዚያም ቀን ከመካከላቸው ሁለት ሰዎች ከኢየሩሳሌም ስድሳ ምዕራፍ ያህል ወደምትርቀው ኤማሁስ ወደምትባለው መንደር ሄዱ፡፡

የትንሣኤ የማሕሌት ምንባብ 2 (ማር.16፥1-ፍጻሜ )

ሰንበትም ባለፈች ጊዜ ማርያም መግደላዊት፥ የያዕቆብ እናት ማርያም፥ ሰሎሜም መጥተው ሥጋዉን ሊቀቡ ሽቱ ገዙ፡፡ በእሑድ ሰንበትም እጅግ ማልደው ፀሐይ በወጣ ጊዜ፥ ወደ መቃብር ሄዱ፡፡ እርስ በርሳቸውም፥ “ድንጋዪቱን ከመቃብሩ አፍ ላይ ማን ያነሣልናል?” አሉ፤ ድንጋዪቱ እጅግ ታላቅ ነበረችና፡፡ አሻቅበውም በተመለከቱ ጊዜ ደንጋዪቱ ተንከባልላ አዩ፡፡ ወደ መቃብሩም በገቡ ጊዜ አንድ ጎልማሳ ነጭ ልብስ ለብሶ በስተቀኝ ተቀምጦ አገኙና ደነገጡ፡፡ እርሱም እንዲህ አላቸው፥ “አትደንግጡ፤ የተሰቀለውን የናዝሬቱን ኢየሱስን ትሻላችሁን? ተነሥቶአል፤ በዚህስ የለም፤ የተቀበረበትም ቦታ እነሆ፡፡ ነገር ግን፥ ሂዱና ለደቀ መዛሙርቱና ለጴጥሮስም ወደ ገሊላ እንደሚቀድማቸው ንገሩቸው፤ እንደ ነገራቸውም በዚያ ያዩታል፡፡” ከመቃብርም ወጥተው ሸሹ፤ ፍርሀትና ድንጋጤ ይዞአቸዋልና፤ ስለፈሩም ለማንም አልተናገሩም፤ ያዘዛቸውንም ሁሉ ለጴጥሮስና ለወንድሞቹ ተናገሩ፡፡ ጌታችን ኢየሱስም ከሙታን ተለይቶ ከተነሣ በኋላ ተገለጠላቸውና፥ ለዘለዓለም ሕይወት የሚሆን የማይለወጥ ቅዱስ ወንጌልን ለፍጥረቱ ሁሉ ከምሥራቅ እስከ ምዕራብ ይሰብኩ ዘንድ ላካቸው፡፡
በእሑድ ሰንበትም ማለዳ ተነሥቶ ሰባት አጋንንትን ላወጣላት ለማርያም መግደላዊት አስቀድሞ ታያት፡፡
እርስዋም ሄዳ ከእርሱ ጋር ለነበሩት ሲያዝኑና ሲያለቅሱ ሳሉ ነገረቻቸው፡፡ እነርሱ ግን ሕያው እንደ ሆነ፥ ለእርስዋም እንደ ተገለጠላት በሰሙ ጊዜ አላመንዋትም፡፡ ከዚህም በኋላ፥ ከእነርሱ ለሁለቱ ወደ ገጠር ሲሄዱ በሌላ መልክ ተገለጠላቸው፡፡ እነርሱም ደግሞ ሄደው ለባልንጀሮቻቸው ነገሩ፤ እነርሱንም ቢሆን አላመኑአቸውም፡፡ ከዚህም በኋላ፥ ደግሞ ዐሥራ አንዱ በማዕድ ተቀምጠው ሳለ ተገለጠላቸው፤ እንደ ተነሣ ያዩትን አላመኑአቸውምና ስለ ሃይማኖታቸው ጒድለት ገሠጻቸው፤ የልባቸውንም ጽናት ነቀፈ፡፡ እንዲህም አላቸው፥ “ወደ ዓለም ሁሉ ሂዱ፤ ለፍጥረትም ሁሉ ወንጌልን ሰበኩ፡፡ ያመነ የተጠመቀም ይድናል፤ ያላመነ ግን ይፈረድበታል፡፡ ይህችም ምልክት በስሜ የሚያምኑትን ትከተላቸዋለች፤ በስሜ አጋንንትን ያወጣሉ፤ በአዲስ ቋንቋም ይናገራሉ፡፡ እባቦችንም በእጃቸው ይይዛሉ፤ የሚጐዳቸውም ነገር የለም፤ የሚገድል መርዝ ቢጠጡም የሚጐዳቸው የለም፤ በድውያን ላይም እጃቸውን ይጭናሉ፤ ድውያኑም ይፈወሳሉ፡፡”
ጌታችን ኢየሱስም ከተነጋገራቸው በኋላ ወደ ሰማይ ዐረገ፤ በአባቱም በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀመጠ፡፡ እነርሱም ወጥተው ጌታ እየረዳቸው፥ ቃሉንም በማያቋርጥ ተአምር እያጸናላቸው በስፍራው ሁሉ አስተማሩ፡፡
ከሰባ ሁለቱ አርድእት አንዲ ወንጌላዊው ማርቆስ የጻፈው ወንጌል ተፈጸመ፤ የጻፈውም በሮም ሀገር በሮማይስጥ ቋንቋ፤ ጌታችን በሥጋ ወደ ሰማይ ባረገ በዐሥራ አንድ ዓመት፥ ቀላውዴዎስ ቄሣር በነገሠ በአራት ዓመት ነው፡፡
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን፡፡ አሜን፡፡

የትንሣኤ የማሕሌት ምንባብ 1 (ማቴ.28፥1-ፍጻሜ )

በሰንበትም ማታ ለእሑድ አጥቢያ ማርያም መግደላዊትና ሁለተኛዋ ማርያም መቃብሩን ሊያዩ መጡ፡፡ እነሆ፥ ታላቅ የምድር መናወጥ ሆነ፤ የእግዚአብሔር መልአክ ከሰማይ ወርዶአልና፤ ቀርቦም በመቃብሩ አፍ ላይ ድንጋይዋን አንከባሎ በላይዋ ተቀመጠ፡፡ መልአኩም እንደ መብረቅ፥ ልብሱም እንደ በረዶ ነጭ ነበረ፡፡ እርሱንም ከመፍራት የተነሣ መቃብሩን የሚጠብቁ ታወኩ፤ እንደ በድንም ሆኑ፡፡ መልአኩም መልሶ ሴቶችን እንዲህ አላቸው፤ “እናንተስ አትፍሩ፤ የተሰቀለውን ኢየሱስን እንደምትሹ አውቃለሁና፡፡ በዚህ የለም፤ እርሱ እንደ ተናገረው ተነሥቶአል፤ ነገር ግን ኑና ተቀብሮበት የነበረውን ቦታ እዩ፡፡ ፈጥናችሁም ሂዱና፡- ከሙታን ተለይቶ ተነሣ፤ እነሆ፥ ወደ ገሊላ ይቀድማችኋል፤ በዚያም ታዩታላችሁ፤ ብላችሁ ለደቀ መዛሙርቱ ንገሩአቸው፤ እነሆም፥ ነገርኋችሁ፡፡” በፍርሀትና በታላቅ ደስታም ከመቃብሩ ፈጥነው ሔዱ፤ ለደቀ መዛሙርቱም ይነግሩአቸው ዘንድ ሮጡ፡፡ እነሆም፥ ጌታችን ኢየሱስ አገኛቸውና፥ “ሰላም ለእናንተ ይሁን” አላቸው፤ እነርሱም ቀርበው እግሩን ይዘው ሰገዱለት፡ ከዚህም በኋላ ጌታችን ኢየሱስ እንዲህ አላቸው፥ “አትፍሩ ሒዱና ወደ ገሊላ እንዲሄዱ ለወንድሞቼ ንገሩአቸው፤ በዚያም ያዩኛል፡፡”
እነርሱም ከሔዱ በኋላ ጠባቂዎች ወደ ከተማ ገብተው የሆነውን ሁሉ ለካህናት አለቆች ነገሩ፡፡ ተሰብስበውም ከሽማግሌዎች ጋር መክረው ለጭፍሮች ብዙ ገንዘብ ሰጡአቸው፡፡ እንዲህም አሏቸው፥ “ተኝተን ሳለን ደቀ መዛሙርቱ በሌሊት መጥተው ሰረቁት በሉ፡፡ ይህም ነገር በገዢው ዘንድ የተሰማ እንደ ሆነ እኛ እናሳምነዋለን፤ እናንተንም ያለ ሥጋት እንድትኖሩ እናደርጋለን፡፡” ጭፍሮችም ገንዘቡን ተቀብለው እንደ አስተማሩአቸው አደረጉ፤ ይህም ነገር እስከ ዛሬ ድረስ በአይሁድ ዘንድ ሲነገር ይኖራል፡፡
ዐሥራ አንዱ ደቀ መዛሙርት ግን ጌታችን ኢየሱስ ወደ አዘዛቸው ተራራ ወደ ገሊላ ሄዱ፡፡ ባዩትም ጊዜ ሰገዱለት፤ እኩሌቶቹ ግን ተጠራጠሩ፡፡ ጌታችን ኢየሱስም ቀርቦ እንዲህ ሲል ተናገራቸው፥ “ሥልጣን ሁሉ በሰማይና በምድር ተሰጠኝ፡፡ እንግዲህ ሂዱና በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው አሕዛብን ሁሉ አስተምሩ፡፡ ያዘዝኋችሁንም እንዲጠብቁ አስተምሩአቸው፤ እኔም እስከ ዓለም ፍጻሜ በዘመኑ ሁሉ ከእናንተ ጋር እኖራለሁ፡፡”
ከዐሥራ ሁለቱ ሐዋርያት አንዱ ሐዋርያ ማቴዎስ በምድረ ፍልስጥኤም በዕብራይስጥ ቋንቋ የጻፈው ወንጌል ተፈጸመ፤ መንፈስ ቅዱስ እያተጋው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሥጋ ወደ ሰማይ ካረገ በኋላ በስምንተኛው ዓመት፤ ቀላውዴዎስ ቄሣር በነገሠ በመጀመሪያዉ ዓመት ጻፈው፡፡
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን፡፡ አሜን፡፡

የሆሣዕና ምንባብ17(ዮሐ.5÷11-31)

እርሱም መልሶ÷ “ያዳነኝ እርሱ፡- አልጋህን ተሸክመህ ሂድ አለኝ” አላቸው፡፡ አይሁድም÷ “አልጋህን ተሸክመህ ሂድ ያለህ ሰውዬው ማነው?” ብለው ጠየቁት፡፡ ያ የተፈወሰው ግን ያዳነው ማን እንደ ሆነ አላወቀም፤ ጌታችን ኢየሱስ በዚያ ቦታ በነበሩት ብዙ ሰዎች መካከል ተሰውሮ ነበርና፡፡ ከዚህም በኋላ ጌታችን ኢየሱስ ያን የዳነውን ሰው በቤተ መቅደስ አገኘውና÷ “እነሆ÷ ድነሃል፤ ግን ከዚህ የባሰ እንዳያገኝህ ደግመኛ እንዳትበድል ተጠንቀቅ” አለው፡፡ ያም ሰው ሄዶ ያዳነው ጌታችን ኢየሱስ እንደ ሆነ ለአይሁድ ነገራቸው፡፡  ስለዚህም አይሁድ ጌታችን ኢየሱስን ያሳድዱትና ሊገድሉትም ይሹ ነበር፤ በሰንበት እንዲህ ያደርግ ነበርና፡፡ ስለዚህም አይሁድ ሊገድሉት በጣም ይፈልጉ ነበር፤ “ሰንበትን የሚሽር ነው” በማለት ብቻ አይደለም ደግሞም እግዚአብሔርን “አባቴ ነው ይላል፤ ራሱንም ከእግዚአብሔር ጋር ያስተካክላል” በማለት ነው እንጂ፡፡

ከዚህም በኋላ ጌታችን ኢየሱስ መልሶ እንዲህ አላቸው÷ “እውነት እውነት እላችኋለሁ፤ ወልድ ከራሱ ብቻ ምንም ሊያደርግ አይችልም፤ አብ ሲያደርግ ያየውን ነው እንጂ፤ ወልድም አብ የሚሠራውን ያንኑ እንዲሁ ይሠራል፡፡ አብ ልጁን ይወዳልና የሚሠራውንም ሥራ ሁሉ ያሳየዋል፤ እናንተም ታደንቁ ዘንድ ከዚህ የሚበልጥ ሥራን ያሳየዋል፡፡ አብ ሙታንን እንደሚያስነሣቸው÷ ሕይወትንም እንደሚሰጣቸው እንዲሁ ወልድም ለሚወድዳቸው ሕይወትን ይሰጣል፡፡ አብ ከቶ በማንም አይፈርድም፤ ፍርዱን ሁሉ ለወልድ ሰጠው እንጂ፡፡ ሰዎች ሁሉ አብን እንደሚያከብሩ ወልድን ያከብሩ ዘንድ፤ ወልድን የማያከብር ግን የላከውን አብን አያከብርም፡፡ እውነት እውነት እላችኋለሁ፤ ቃሌን የሚሰማ በላከኝም የሚያምን የዘለዓለም ሕይወትን ያገኛል፤ ከሞትም ወደ ሕይወት ተሻገረ እንጂ ወደ ፍርድ አይሄድም፡፡

“እውነት እውነት እላችኋለሁ፤ ሙታን የእግዚአበሔርን ልጅ ቃል የሚሰሙበት ሰዓት ይመጣል፤ እርሱም አሁን ነው፤ የሚሰሙትም ይድናሉ፡፡ ለአብ በራሱ ሕይወት እንዳለው÷ እንዲሁም ደግሞ ለወልድ በራሱ ሕይወት እንዲኖረው ሰጠው፡፡ የእግዚአብሔር ልጅ የሰው ልጅ ነውና ይፈርድ ዘንድ ሥልጣንን ሰጠው፡፡

“በመቃብር ያሉ ሁሉ ቃሉን የሚሰሙባት ጊዜ ትመጣለችና ስለዚህ አታድንቁ፡፡ መልካም የሠሩ ለሕይወት ትንሣኤ÷ ክፉ የሠሩም ለፍርድ ትንሣኤ ይነሣሉ፡፡ እኔ ከራሴ አንዳች አደርግ ዘንድ አልችልም፤ እንደ ሰማሁ እፈርዳለሁ እንጂ፤ ፍርዴም እውነት ነው፤ የላከኝን ፈቃድ እንጂ የእኔን ፈቃድ አልሻምና፡፡

 

የሆሣዕና ምንባብ16(ሐዋ.28÷11-ፍጻ.)

 ከሦስት ወር በኋላም በዚያች ደሴት ወደ ከረመችው ወደ እስክንድርያ መርከብ ወጣን፤ በዚያች መርብ ላይም የዲዮስቆሮስ ምልክት ነበረባት፤ ይኸውም “የመርከበኞች አምላክ” የሚሉት ነው፡፡ ከዚያም ሄደን ወደ ሰራኩስ ደረስን፤ በዚያም ሦስት ቀን ተቀመጥን፡፡ ከዚያም ሄደን ሬቅዩን ወደምትባል ሀገር ደረስን፤ በማግሥቱም ወጣን፤ ከአንድ ቀንም በኋላ ከጐንዋ ነፋስ በነፈሰ ጊዜ በሁለተኛው ቀን ወደ ፑቲዮሉስ ደረስን፡፡ በዚያምም ወንድሞችን አግኝተን ተቀበሉን፤ በእነርሱ ዘንድም ሰባት ቀን እንድንቀመጥ ለመኑን፤ ከዚያም በኋላ ሄደን ወደ ሮሜ ደረስን፡፡ በዚያም ያሉት ወንድሞች ስለ እኛ በስሙ ጊዜ፤ አፍዩስ ፋሩስ እስከሚባለው ገበያና እስከ ሦስተኛው ማረፊያ ድረስ ወጥተው ተቀበሉን፤ ጳውሎስም ባያቸው ጊዜ እግዚአብሔርን አመሰገነ፤ ልቡም ተጽናና፡፡  ወደ ሮሜም በገባን ጊዜ የመቶ አለቃው እስረኞችን ለሠራዊቱ አለቃ አስረከበ፤ ጳውሎስ ግን ከሚጠብቀው አንድ ወታደር ጋር ለብቻው ይቀመጥ ዘንድ ፈቀደለት፡፡

ከሦስት ቀንም በኋላ ጳውሎስ የአይሁድን ታላላቅ ሰዎች ሰበሰባቸው፤ በተሰበሰቡም ጊዜ እንዲህ አላቸው÷ “ወንድሞቻችን ሆይ÷ እኔ በሕዝቡም ላይ ቢሆን÷ በአባቶቻችንም ሕግ ላይ ቢሆን ያደረግሁት ክፉ ነገር የለም፤ ነገር ግን በኢየሩሳሌም እንደ ታሰርሁ ለሮም ሰዎች አሳልፈው ሰጡኝ፡፡ እነርሱም መርምረው ለሞት የሚያበቃ በደል ስለአላገኙብኝ በተነሡ ጊዜ ወደ ቈሣር ይግባኝ ለማለት ግድ ሆነብኝ፤ ነገር ግን ወገኖቼን የምከስበት ነገር ኖሮኝ አይደለም፡፡ ስለዚህም ላያችሁ÷ ልነግራችሁና ላስረዳሁ ወደ እኔ እንድትመጡ ማለድኋችሁ፤ ስለ እሰራኤል ተስፋ በዚህ ሰንሰለት ታስሬአለሁና፡፡” የአይሁድ ታላላቅ ሰዎችም እንዲህ አሉት÷ “ለእኛስ ከይሁዳ ሀገር ስለ አንተ መልእክት አልደረሰንም፤ ከኢየሩሳሌም ከመጡት ወንድሞችም ቢሆን አንድ ስንኳ ከዚህ አስቀድሞ ስለ አንተ ክፉ ነገር ያወራን÷ የነገረንም የለም፡፡ ነገር ግን በዚህ ነገር በየስፍራው ሁሉ እንዲጣሉ በእኛ ዘንድ ታውቋልና የአንተን ዐሳብ ደግሞ ከአንተ እንሰማ ዘንድ እንወድዳለን፡፡” ከዚህም በኋላ ወደ እርሱ የሚመጣበትን ቀን ቀጠሩትና ብዙዎች ወዳረፈበት ወደ እርሱ መጡ፤ ከጥዋትም ጀምሮ እስከ ማታ ድረስ ስለ እግዚአብሔር መንግሥት እየመሰከረ ስለ ጌታችን ስለ ኢየሱስም ከሙሴ ኦሪትና ከነቢያት እየጠቀሰ ነገራቸው፡፡ ከእነርሱም እኩሌቶቹ የተናገረውን አመኑ፤ እኩሌቶቹ ግን አልተቀበሉትም፡፡ እርስ በርሳቸውም ባልተስማሙ ጊዜ ጳውሎስ አንዲት ቃል ከተናገረ በኋላ ከእርሱ ተመለሱ፤ እንዲህም አላቸው÷ “መንፈስ ቅዱስ በነቢዩ በኢሳይያስ አንደበት ለአባቶቻችን በእውነት እንዲህ ብሎ መልካም ነገር ተናግሮአ፡፡ ‹ወደዚህ ሕዝብ ሂድና እንዲህ በላቸው፡- መስማትን ትሰማላችሁ፤ ግን አታስተውሉም፤ ማየትንም ታያላችሁ፤ ግን አትመለከቱም፡፡ በዐይናቸው እንዳያዩ÷ በጆሮአቸውም እንዳይሰሙ÷ በልባቸውም እንዳያስተውሉ÷ ወደ እኔም እንዳይመለሱና ይቅር እንዳልላቸው የዚህ ሕዝብ ልባቸው ደንድኖአልና÷ ጆሮአቸውም ደንቁሮአልና÷ ዐይናቸውንም ጨፍነዋልና›፡፡ እንግዲህ ከእግዚአብሔር የተገኘች ይህቺ ድኅነት ለአሕዛብ እንደምትሆን ዕወቁ፤ እነርሱም ይሰሙታል፡፡” ይህንም በተናገራቸው ጊዜ አይሁድ እርስ በርሳቸው እጅግ እየተከራከሩ ወጥተው ሄዱ፡፡ ጳውሎስም በገንዘቡ በተከራየው ቤት ሁለት ዓመት ተቀመጠ፤ ወደ እርሱ የሚመጣውንም ሁሉ ይቀበል ነበር፡፡ ማንም ሳይከለክለው የእግዚአብሔርን መንግሥት ይሰብክ ነበር፤ ስለ ጌታችን ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ እጅግ ገልጦ ያስተምር ነበር፡፡ ጳውሎስም በመጀመሪያ ጊዜ ወደ ኔሮን ቄሣር ገብቶ ነበርና ረትቶ በሰላም ሄደ፤ ከዚህም በኋላ ሁለት ዓመት ኖሮ ከሮም ወጣ፡፡ ከዚህም በኋላ ወደ ሮም ተመልሶ የኔሮን ቄሣር ዘመዶችን አጠመቀ፤ በኔሮን ትእዛዝም በሰይፍ ተመትቶ መከራውንም ታግሦ ሰማዕት ሆነ፡፡