የሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ክብረ በዓል

ከመጽሐፈ ስንክሳር

ሰኔ ፲፩ ቀን ፳፻፲፫ ዓ.ም

አንድ አምላክ በኾነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሰኔ ዐሥራ ሁለት በዚች ዕለት የከበረ የመላእክት አለቃ የመልአኩ የሚካኤል የመታሰቢያውን በዓል ያከብራሉ፡፡ የሚያከብሩበትም ምክንያት እንዲህ ነው፤

እስክንድርያ በምትባል ከተማ አክላወበጥራ የተባለች ንግሥት የንጉሥ በጥሊሞስ ልጅ ዙሐል በሚባል ኮከብ ስም ያሠራችው ታላቅ ምኵራብ ነበረና በየዓመቱ ሰኔ በባተ በዐሥራ ሁለት ቀን በዚያ ምኵራብ ሕዝቡ ተሰብስቦ ታላቅ በዓል ያደርጉ ነበር፡፡ በዚያም ምኵራብ ውስጥ ዙሐል የሚሉት ታላቅ የነሐስ ጣዖት ነበረና በዓሉ በሚከበርበት ዕለት ብዙ ፍሪዳዎችን ያርዱለት ነበር፡፡

አባ እለእስክንድሮስ እስከተሾመበት ዘመን ድረስ ለዚያ ጣዖት እንዲህ ሲያደርጉ ኖሩ፡፡ ይኸውም ሦስት መቶ ዓመተ ምሕረት ተፈጽሞ በአራተኛው ምዕት ውስጥ ነበር፡፡ አባ እለእስክንድሮስ በእስክንድርያ ከተማ ሊቀ ጵጵስና በተሾመ ጊዜ፣ ጻድቅ ቆስጠንጢኖስም በነገሠ ጊዜ የክርስትና ሃይማኖት ስለ ተስፋፋች ያን ጣዖት ሊሠብረው ወድዶ ሳለ ጐስቋሎች ሰዎች ከለከሉት፡፡ እንዲህም አሉት፤ ‹‹እኛ በዚህ ቦታ ይህን በዓል ማክበርን ለምደናል፡፡ እነሆ ከአንተ በፊት ዐሥራ ስምንት ሊቃነ ጳጳሳት አልፈዋል፤ ይህን ልማዳችንንም አልለወጡብንም፡፡››

አባ እለእስክንድሮስ ግን ገሠፃቸው፤ አስተማራቸው፡፡ ስሕተታቸውንም በመግለጥ እንዲህ አላቸው፤ ‹‹ይህ ጣዖት የማይጎዳና የማይጠቅም ነው፡፡ እርሱንም የሚያመልክ ሰይጣናትን ያመልካቸዋል፡፡ ምክሬንስ ብትሰሙ ቀድሞ እንደ ነበረ አድርጌ ይህን በዓል እሠራላችኋለሁ፤ ይኸውም ጣዖቱን እንድንሰብረው፣ ምኵራቡንም እንድንባርከውና በከበረ መልአክ በመላእክት አለቃ በሚካኤል ስም ቤተ ክርስቲያን አድርገን እንድንሰይመው ነው፡፡ እኛም ይህን ታላቅ በዓል እንሠራለን፡፡ የሚታረዱትም ላሞችና በጎች ለድኆችና ለጦም አዳራዎች፣ ለችግረኞችም በከበረው መልአክ ስም ምግብ ይኹኑ፡፡ እርሱ በእግዚአብሔር ዘንድ ባለሟልነት ያለው ስለ ኾነ ስለ እኛ ይማልዳልና፡፡›› ይህንንም ብሎ በዚህ በጎ ምክር አስወደዳቸው፤ እነርሱም ታዘዙለት፡፡

ከዚህም በኋላ ያንን ምኵራብ አድሰው በዚህ የከበረ መልአክ የመላእክት አለቃ ሚካኤል ስም ቤተ ክርስቲያን አደረጉት፡፡ በዚችም ዕለት አከበሩዋት፡፡ እርሷም የታወቀች ናት፡፡ እስላሞችም እስከ ነጉሡበት ዘመን ኑራ ከዚያ በኋላ አፈረሱዋት፡፡ ይህም በዓል ተሠራ፤ እስከ ዛሬም ጸንቶ ይኖራል፡፡

ዳግመኛም በዚች ዕለት እግዚአብሔር የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤልን በነገዱ ውስጥ በመላእክት ዅሉ ላይ በብዙ ክብር ሾመው፡፡ ይህም የከበረ መልአክ ክብር ይግባውና በጌታችን ፊት ስለ ሰው ልጆችና ስለ ፍጥረትም ዅሉ ይለምናል፤ ይማልዳልም፡፡ የዚህ የከበረ የመላእክት አለቃ ሚካኤል ተአምራቱ ብዙዎች ናቸው፡፡ ከእነርሱም አንዱ ይህ ነው፤

እግዚአብሔርን የሚፈራ አንድ ሰው ነበረ፡፡ እርሱም የከበረ የሚካኤልን የበዓሉን መታሰቢያ በየወሩ በዐሥራ ሁለተኛው ቀን ይልቁንም በሰኔ እና በኅዳር ወር አብልጦ ያከብር ነበር፡፡ በጐረቤቱም ርኅራኄ የሌለው አንድ ባለ ጠጋ ሰው ነበረ፡፡ ይህን እግዚአብሔርን የሚፈራውን ሰው የከበረ መልአክ የሚካኤልን በዓል በሚያደርግበት ጊዜ ይጠላውና ያቃልለው ነበር፡፡ ለድኆች ስለ መራራቱም ይዘባበትበት ነበረ፡፡ የሕይወቱ ዘመንም ተፈጽሞ የሚሞትበትና ከዚህ ከኃላፊው ዓለም ድካምም የሚያርፍበት ጊዜ ሲቀርብ የክቡር መልአክ ሚካኤልን የበዓሉን መታሰቢያ ታደርግ ዘንድ፣ ምጽዋት ሰጭም ትኾን ዘንድ ሚስቱን አዘዛት፡፡ ከዚህም በኋላ ዐረፈና ገንዘው ቀበሩት፡፡

ሚስቱም ፀንሳ ነበረች፡፡ የመውለጃዋ ጊዜም ደርሶ ምጥ ያዛት፡፡ በታላቅ ጭንቀት ውስጥ ሳለችም እንዲህ ብላ ጸለየች፤ ‹‹የእግዚአብሔር መልአኩ ሆይ ራራልኝ፡፡ በእርሱ ዘንድ ባለሟልነት አለህና፡፡ በእግዚአብሔር ዘንድ ስለ እኔ ለምንልኝ፡፡›› ይህንንም በአለች ጊዜ በቤቷ ውስጥ ብርሃን በራ፡፡ ከችግርም ዳነች፤ መልአኩ ውብ የኾነ ወንድ ልጅንም ወለደች፡፡ የእግዚአብሔርም መልእክተኛ ቅዱስ ሚካኤል ከሰማይ ወርዶ ሕፃኑን እንዲህ ብሎ ባረከው፤ ‹‹ርኅራኄ የሌለውን የዚህን ባለጠጋ ገንዘብና ሀብት፣ ጥሪቱንም ዅሉ ይህ ሕፃን እንዲወርስ እግዚአብሔር አዝዟል፡፡››

ባለ ጠጋውም በቤቱ፣ በዐልጋው ላይ ሳለ ጌታ ጆሮውን ከፍቶለት ይህን ነገር ከመልአኩ ሰማ፡፡ ይህንን በሰማ ጊዜ ታላቅ ኀዘን ደረሰበት፡፡ ሕፃኑንም የሚገድልበትን ምክንያት ይፈልግ ጀመረ፡ ነገር ግን ክብር ይግባውና ጌታ ይጠብቀው ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ ያ ባለጠጋ ምክንያት አዘጋጅቶ ‹‹የሚያገለግለኝ ልጅ ይኾነኝ ዘንድ ልጅሽን ስጪኝ፡፡ እኔም እየመገብኹና እያለበስኹ አሳድገዋለሁ፡፡ ለአንቺም ሃያ ወቄት ወርቅ እሰጥሻለሁ›› አላት፡፡ ይህንንም ነገር ከባለጠጋው በሰማች ጊዜ ስለ ችግሯ እጅግ ደስ አላት፡፡ ልጅዋንም ሰጠችው፡፡ እርሱም ሃያውን ወቄት ወርቅ ሰጣት፡፡ ልጅዋንም ወሰደው፡፡ የምሻው ተፈጸመልኝ ብሎ ደስ አለው፡፡

ከዚህም በኋላ በልጁ ቁመት ልክ ሣጥን አሠርቶ ሕፃኑን በሣጥኑ ውስጥ አስገብቶ ዘጋበት፡፡ እስከ ባሕርም ተሸክመው ወስደው በባሕር ጣሉት፡፡ ክብር ይግባውና በጌታችን ፈቃድ ያ ሣጥን ሳይሠጥም ከዚያች አገር የሃያ ቀን መንገድ ያህል ርቃ ወደምትገኝ ወደ አንዲት አገር ወደብ እስከሚደርስ በባሕሩ ላይ ተንሳፈፈ፡፡ በባሕሩም አካባቢ በጎቹን አሰማርቶ የሚጠብቅ አንድ ሰው ነበርና ሣጥኑን በውኃ ላይ ተንሳፎ አየው፡፡ እርሱም ከባሕሩ አውጥቶ ወደ ቤቱ ወሰደው፡፡ ይህን ሣጥን እንዴት እንደሚከፍተው ያስብ ጀመረ፡፡ ይህንም ሲያስብ ወደ ባሕሩ ይሔድ ዘንድ ጌታችን በልቡናው ሐሳብ አሳደረበት፡፡ ወዲያውኑም ተነሥቶ ወደ ባሕሩ ሔደና አንድ ዓሣ የሚያጠምድ ሰው አገኘ፡፡

ዓሣ አጥማጁንም ‹‹መረብህን በኔ ስም ጣል፡፡ ለሚያዘውም ዓሣ ዋጋውን እሰጥሃለሁ›› አለው፡፡ አጥማጁም እንዳለው አደረገ፡፡ ያን ጊዜም ታላቅ ዓሣ ተያዘ፡፡ ዋጋውንም ይዞ ወደ ቤቱ ሔደ፡፡ ለራትም ይጠብሰው ዘንድ አረደው፡፡ በሆዱም ውስጥ መክፈቻ አገኘ፡፡ በልቡም ‹‹ይህ መክፍቻ ይህን ሣጥን ይከፍተው ይኾን?›› አለ፡፡ በሣጥኑ ቀዳዳም በአስገባው ጊዜ ፈጥኖ ተከፈተ፡፡ በውስጡም ይህን ታናሽ ብላቴና አገኘ፡፡ ልጅ የለውም ነበርና ታላቅ ደስታ ደስ አለው፡፡ ጌታችንንም አመሰገነው፡፡ ሕፃኑንም በመልካም አስተዳደግ አሳደገው፡፡ ሕፃኑም አድጎ ጐልማሳ ኾነ፡፡

ከብዙ ዘመናትም በኋላ ያ ባለ ጠጋ ተነሥቶ ወደዚያ አገር ሔደ፡፡ በመሸም ጊዜ ወደ በግ ጠባቂው ደጅ ደረሰ፡፡ በግ ጠባቂውን ‹‹እስከ ነገ የምናድርበት ማደሪያ በአንተ ዘንድ እናገኛለን? ኪራዩንም እሰጥሃለሁ›› አለው፡፡ በግ አርቢውም ‹‹እንዳልኽ ይኹንና እደር›› አለው፡፡ ባለ ጠጋውም በዚያ አደረ፡፡ ራት በሚቀርብም ጊዜ ሕፃኑን ‹ባሕራን› ብሎ ጠራው፡፡ ባለ ጠጋውም ሰምቶ ‹‹ልጅህ ነውን?›› ብሎ ጠየቀው፡፡ በግ ጠባቂውም ‹‹አዎን፤ ታናሽ ሕፃን ኾኖ ሳለ ከባሕር አግኝቼዋለሁና እግዚአብሔር የሰጠኝ ልጄ ነው›› አለው፡፡ ባለ ጠጋውም ‹‹በምን ዘመን አገኘኸው?›› አለው፡፡ እርሱም ‹‹ከሃያ ዓመት በፊት›› ብሎ መለሰለት፡፡ ያን ጊዜም እርሱ ወደ ባሕር የጣለው መኾኑን ዐውቆ እጅግ አዘነ፡፡

በማግሥቱም ጎዳናውን ሊጓዝ በተነሣ ጊዜ ሰይጣናዊ ምክንያት አመካኝቶ በግ ጠባቂውን እንዲህ አለው፤‹‹ዕገሊት ወደምትባል አገር በቤቴ የረሳሁት ጉዳይ ስላለ እንድልከው ልጅህን ትሰጠኝ ዘንድ እሻለሁ፡፡ እኔም የድካም ዋጋውን ሃያ ወቄት ወርቅ እሰጥሃለሁ›› አለው፡፡ የብላቴናውም አባት ስለ ገንዘቡ ደስ ብሎት ልጁ ባሕራንን ሰጠው፡፡ እንዲህም ብሎ አዘዘው፤ ‹‹ልጄ ባሕራን፣ ይህ የከበረ ሰው ስለ ጉዳዩ ወደ ቤቱ ይልክህ ዘንድ ና፤ ወደ ቤትህም በሰላም ትመለሳለህ፡፡››

ያን ጊዜም ባለ ጠጋው ወደ መጋቢው እንዲህ ብሎ ደብዳቤ ጻፈ፤ ‹‹ይቺን ደብዳቤ በምታነባት ጊዜ ደብዳቤዋን ይዞ የመጣውን ገድለህ በጉድጓድ ውስጥ ጣለው፡፡ ማንም ዐይወቅ፡፡›› በመካከላቸውም የሚተዋወቁበትን ምልክት ጽፎ አሸጋት፤ ለባሕራንም ሰጠው፡፡ ለመንገዱም የሚኾነውን ስንቅ ሰጠው፡፡ ባሕራንም ተነሥቶ ጉዞውን ጀመረ፡፡ ሲጓዝም ሰንብቶ የአንዲት ቀን ጉዞ ሲቀረው እነሆ የመላእክት አለቃ የከበረ መልአክ ሚካኤል በንጉሥ ጭፍራ አምሳል በነጭ ፈረስ ላይ ተቀምጦ ‹‹አንተ ጐልማሳ የያዝኸው ምንድነው›› አለው፡፡ ‹‹ወደ ዕገሌ አገር ወደ ቤቱ ለማድረስ ከአንድ ባለ ጠጋ የተጻፈች መልእክት ናት›› አለው፡፡ ‹‹ያቺን ደብዳቤ አሳየኝ›› አለው፤ እርሱም ስለ ፈራ ሰጠው፡፡

በዚያን ጊዜም የከበረው መልአክ ሚካኤል ያቺን የሞት መልእክት ደመሰሳት፡፡ በእርሷ ፈንታም በንፍሐት ለውጦ እንደህ ብሎ ጻፈ፤ ‹‹ይቺን ደብዳቤ ይዞ ለመጣ ባሕራን ለሚባል ሰው ይቺ ደብዳቤደርሳ በምትነበብበት ጊዜ ልጄ ዕገሊትን አጋቡት፡፡ በውስጥና በውጭ ያለ ንብረቴንና ጥሪቴን፣ ወንዶችና ሴቶች ባሮቼን፣ ጠቅላላ ንብረቴንም አውርሼዋለሁና የፈለገውንም ሊያደርግ ሥልጣን ሰጥቼዋለሁና እኔን አትጠብቁኝ፡፡ እኔ ብዙ እዘገያለሁ የኔ ሹም እገሌ ሆይ! በእኔና በአንተ መካከል ይቺ ምልክት እነኋት፡፡››

ከዚህ በኋላ አሽጐ ለባሕራን ሰጠውና ‹‹ወደ ባለ ጠጋው ቤት ሂደህ ይቺን ደብዳቤ ለሹሙ ስጠው፡፡ በጎዳናም እኔ እንደ ተገናኘሁህ አትንገረው፡፡ እንዳይገድልህም ይህን የሞት ደብዳቤ ለውጬልሃለሁ›› አለው፡፡ ባሕራንም ‹‹እሺ ጌታዬ ያዘዝኸኝን ዅሉ አደርጋለሁ›› አለ፡፡

ባሕራንም ወደ ባለ ጠጋው ቤት በደረሰ ጊዜ ያቺን ደብዳቤ ለሹሙ ሰጠው፡፡ በአነበባት ጊዜ በመካከላቸው ያለውን ምልክት አገኘ፡፡ አስተውሎም እርግጠኛ እንደ ኾነ ዐወቀ፡፡ ከዚህም በኋላ ለባሕራን ሠርግ አዘጋጅቶ እንደሚገባ በቤተ ክርስቲያን ሥርዓት በተክሊል የባለ ጠጋውን ልጅ አጋቡት፡፡ ዐርባ ቀን ያህልም ደስታና ሐሴት እያደረጉ ኖሩ፡፡ ከዚህ በኋላ ባለ ጠጋው ከሔደበት መመለሻው ጊዜ ኾኖ በደስታ የኾነውን የመሰንቆና የእንዚራ ድምፅ ሰምቶ ‹‹ይህ የምሰማው ምንድነው›› ብሎ ጠየቀ፡፡

እነርሱም ‹‹ስሙ ባሕራን ለተባለ የአንተን ደብዳቤ ላመጣ ጐልማሳ ሰው ልጅህ ዕገሊትን አጋቡት፡፡ እነሆ ለዐርባ ቀናት በሠርግ ላይ ነው፡፡ ገንዘብህንና ጥሪትህን ዅሉ ወንዶችና ሴቶች ባሮችህን አንተ እንዳዘዝኽ ሰጥተውታል›› አሉት፡፡ ይህንም በሰማ ጊዜ ደንግጦ ከፈረሱ ላይ ወደቀ በድንገትም ሞተ፡፡

ባሕራንም በጎ ሥራዎችን የሚሠራ ኾነ፡፡ የተገለጠለትና ከመገደል ያዳነው የመላእክት አለቃ የከበረ መልአክ ሚካኤል እንደ ኾነ፤ ሊገድለው የሚሻውን የባለ ጠጋውን ጥሪቱን ዅሉ ያወረሰውም እርሱ እንደ ኾነ ተረዳ፡፡ የዚህንም የከበረ መልአክ የመላእክት አለቃ ሚካኤልን መታሰቢያ በየወሩ ያደርግ ጀመረ፡፡ ቤተ ክርስቲያንም ሠራለት፡፡ የቅዱስ ሚካኤልን ሥዕሉን አሥሎ በቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ አደረገው፡፡ ከእርሱም ብዙዎች ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ፡፡ ባሕራንም ቅስና ተሹሞ እስከ ዕለተ ሞቱ በዚያች ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሚያገለግል ኾኖ ኖረ፡፡ በዚህ በከበረ የመልአክት አለቃ ሚካኤል አማላጅነት ከእናቱና ከአባቱ፣ ከልጆቹም ጋራ የዘለዓለም ሕይወትን ወረሰ፡፡

መድኃኒታችን በተነሣባትም ቀን ይህ ክቡር መልአክ ሚካኤል ከውስጠኛው መጋረጃ ውስጥ ገብቶ በክብር ባለቤት ፊት እንዲህ እያለ ይለምናል፤ ‹‹እውነት ስለ ኾነ ቃል ኪዳንህ በምድር መታሰቢያዬን የሚያደርጉትን ትምርልኝ ዘንድ፤ ፈጣሪዬ ሆይ! እኔ አገልጋይኅና መልእክተኛህ ከቸርነትህ እለምናለሁ፡፡ አንተ መሐሪና ይቅር ባይ ነህና፡፡›› የክብር ባለቤት ጌታችንም እንዲህ ብሎ ይመልስለታል፤ ‹‹የመንፈሳውያን ሰማያውያን መላእክት አለቃቸው ሚካኤል ሆይ! መታሰቢያህን የሚያደርገውን ዅሉ መሸከም እንደምትችል ከሲኦል ሦስት ጊዜ በክንፎችህ ተሸክመህ እንድታወጣ እነሆ እኔ አዝዤሃለሁ፡፡››

ይህንንም ቃል በሰማ ጊዜ እጅግ ደስ ብሎት የበዓሉን መታሰቢያ ከሚያደርጉት በክንፎቹ ተሸክሞ የእሳቱን ባሕር አሳለፋቸው፡፡ እነርሱንም ከብቻው ጌታ በቀር የሚቈጥራቸው የለም፡፡ስለዚህም የዚህን ታላቅ የከበረ የመላእክት አለቃ ሚካኤልን የበዓሉን መታሰቢያ ለማድረግ መታገል ይገባናል፡፡ እርሱ ከሰይጣን ወጥመድ ያድነን ዘንድ በዘመናችን ዅሉም ይጠብቀን ዘንድ፤ ኀጢአታችንንም ያስተሰርይ ዘንድ፤ መከራችንንም ያርቅ ዘንድ፤ የምድራችንንም ፍሬ ይባርክ ዘንድ፤ ፈቃዱንም ለመሥራት ይረዳን ዘንድ፤ ከእኛ ወገን የሞቱትን ዕረፍተ ነፍስ ይሰጥ ዘንድ፤ ወደ መንገድ የሔዱ አባቶቻችንና ወንድሞቻተንን ወደ ቤቶቻቸው በሰላም፣ በጤና ይመልሳቸው ዘንድ፤ በመካከላችንም ፍቅር ያደርግልን ዘንድ፤ እስከ መጨረሻዪቱም ሕቅታ ድረስ በቀናች ሃይማኖት ያጸናን ዘንድ፤ የክርስቶስ ወገኖች የኾኑ መኳንንቶቻችንንም ጠብቆ በወንበሮቻቸው ላይ ያጸናቸው ዘንድ፤ የሳቱትንም ወደ ቀናች ሃይማኖቱ ይመልሳቸው ዘንድ በእግዚአብሔር ፊት ስለ እኛ ይለምናልና፡፡

ዳግመኛም በዚህች ቀን እግዚአብሔርን የሚፈራ አስተራኒቆስ የሚስቱ የቅድስት አፎምያ የዕረፍቷ መታሰቢያ ኾነ፡፡ ይህም ሰው በየወሩ ሦስት በዓላቶችን እያከበረ ኖረ፡፡ እሊህም ክብር ይግባውና የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የልደቱ መታሰቢያ በየወሩ በሃያ ዘጠኝ፤ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም በዓል መታሰቢያ በየወሩ በሃያ አንድ፤ የከበረ የመላእክት አለቃ የኾነ የቅዱስ ሚካኤል በዓል መታሰቢያም በየወሩ በዐሥራ ሁለት ቀን ናቸው፡፡ የሚሞትበትም ጊዜው ሲቀርብ እርሱ ሲሠራው የነበረውን ምጽዋት ይልቁንም እሊህን ሦስቱን በዓላት እንዳታስታጉል ሚስቱን ቅድስት አፎምያን አዘዛት፡፡

እርሷም የከበረ የመልአኩ የሚካኤልን ሥዕል ያሥልላት ዘንድ ባሏን ለመነችው፡፡ እርሱም አሠርቶ ሰጣትና በቤቷ ውስጥ በክብር አኖረችው፡፡ ባሏም ከዐረፈ በኋላ ባሏ ያዘዛትን መሥራት ጀመረ፡፡ ሰይጣን ግን ቀናባት፡፡ በመበለት ሴት መነኵሲት ተመስሎ ከእርሷ ጋር ተነጋገረ፡፡ እንዲህም አላት፤ ‹‹እኔ አዝንልሻለሁ፤ እራራልሻለሁም፡፡ ገንዘብሽ ሳያልቅ፣ የልጅነትሽም ወራት ሳያልፍ አግብተሽ ልጅ ትወልጂ ዘንድ እመክርሻለሁ፡፡ ባልሽም መንግሥተ ሰማያትን ወርሷል፡፡ ምጽዋትም አይሻም፡፡›› አፎምያም እንዲህ ብላ መለሰችለት፤ ‹‹እኔ ከሌላ ሰው ጋራ ላልገናኝ በእግዚአብሔር ፊት ቃል ኪዳን አድርጌያለሁ፡፡ ርግቦችና መንጢጦች እንኳ ሌላ ባል አያውቁም፡፡ በእግዚአብሔር አርአያ ከተፈጠሩ ሰዎች ይህ ሊኾን እንዴት ይገባል?›› ምክሩንም ባልሰማች ጊዜ አርአያውን ለውጦ በላይዋ ጮኸባት፡፡ እንዲህም አላት፤ ‹‹እኔ በሌላ ጊዜ እመጣለሁ፡፡›› እርሷም የከበረ የመልአኩ የሚካኤልን ሥዕል ይዛ አሳደደችው፡፡ ከዚህም በኋላ ሰኔ ዐሥራ ሁለት ቀን የከበረ የመልአኩ የሚካኤል በዓል በሚከብርበት ዕለት እርሷም የበዓሉን ዝግጅት ስታዘጋጅ ሳለች ብርሃናዊ መልአክ መስሎ መጣ፡፡ ‹‹አፎምያ ሆይ! ሰላም ላንቺ ይኹን! እኔ የመላእክት አለቃ ሚካኤል ነኝ፡፡ ጌታ ወደ አንቺ ልኮኛልና እርሱም ይህን መመጽወትሽን ትተሽ ለአንድ ምእመን ሚስት ትኾኚ ዘንድ አዞሻል፡፡››

ባል የሌላት ሴት መልሕቅ የሌለውን መርከብ እንደምትመስል ዕወቂ፤ እንደ አብርሃምና ያዕቆብ እንደ ዳዊትም እንደነርሱ ያሉ ብዙ ሴቶችን እንዳገባ፤ እግዚአብሔርንም ደስ እንዳሰኙት ከብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ጥቅሶችን ያመጣላት ጀመረ፡፡

ቅድስት አፎምያም መልሳ ‹‹አንተ የእግዚአብሔር መልአክ ከኾንኽ የመስቀል ምልክት ከአንተ ጋር ወዴት አለ? የንጉሥ ጭፍራ የኾነ ዅሉ የንጉሡን ማኅተም ሳይዝ ወደ ሌላ ቦታ አይሔድምና›› አለችው፡፡ ሰይጣኑም ይህንን በሰማ ጊዜ መልኩ ተለወጠና አነቃት፡፡ እርሷም ወደ ከበረው መልአክ ወደ ሚካኤል ጮኸች፡፡ ወዲያውኑም ደርሶ አዳናት፡፡ ያንም ሰይጣን ይዞ ይቀጣው ጀመረ፡፡ ሰይጣኑም ጮኸ፡፡ ‹‹ማረኝ፤ ያለ ጊዜዬ አታጥፋኝ፤ እግዚአብሔር እስከ ዓለም ፍጻሜ ታግሦናልና›› እያለ ለመነው፡፡ ከዚያም ተወውና አባረረው፡፡

የከበረ መልአክ ሚካኤልም እንዲህ አላት፤ ‹‹ብፅዕት አፎምያ ሆይ! ሒደሽ የቤትሽን ሥራ አዘጋጂ፡፡ አንቺ ዛሬ ከዚህ ዓለም በሞት ትለዪአለሸና፡፡ እነሆ እግዚአብሔርም ዐይን ያላየውን፣ ጆሮም ያልሰማውን፣ በሰው ልብም ያልታሰበውን አዘጋጅቶልሻል፡፡›› ይህንንም ብሎ ሰላምታ ሰጣት፡፡ ወደ ሰማያትም ዐረገ፡፡ የበዓሉንም ዝግጅት እንደሚገባ ከፈጸመች በኋለ ወደ ኤጲስቆጶሱና ወደ ካህናቱ ዅሉ ላከች፡፡ ወደ እርሷም በመጡ ጊዜ ለድኆችና ለጦም አዳሪዎች ይሰጧቸው ዘንድ ገንዘቧን ዅሉ አስረከበቻቸው፡፡ ከዚህም በኋላ ተነሥታ ጸለየች፡፡ የከበረ የመልአኩ የቅዱስ ሚካኤልንም ሥዕል አንሥታ ታቅፋ ሳመችው፡፡ ያን ጊዜም በሰላም ዐረፈች፡፡

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይኹን፡፡ እኛንም በጸሎቷ ይማረን፡፡ የዚህም የከበረ መልአክ ሚካኤል የረድኤቱ ኃይል ዅላችን የክርስቲያን ወገኖችን ይጠብቀን፡፡ ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

ምንጭ፡-መጽሐፈ ስንክሳር፣ ሰኔ ፲፪ ቀን፡፡