የዐቢይ ጾም ሳምንታት (ለሕፃናት) – ክፍል ሦስት

በልደት አስፋው

መጋቢት ፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

፭. ደብረ ዘይት

እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች? ስለዅሉም ነገር እግዚአብሔር ይመስገን! ባለፈው ዝግጅታችን አራተኛውን የዐቢይ ጾም ሳምንት የተመለከተ ትምህርት አቅርበንላችሁ ነበር፡፡ ዛሬ ደግሞ ስለ አምስተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት (ስለ ደብረ ዘይት) አጭር ትምህርት ይዘንላችሁ ቀርበናል፡፡ ትምህርቱን በተግባር ላይ እንድታውሉት እሺ? መልካም ልጆች! አሁን በቀጥታ ወደ ትምህርቱ እንወስዳችኋለን፤

ልጆች! እንደምታስታውሱት አምስተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ‹‹ደብረ ዘይት›› ይባላል፡፡ ትርጕሙም ‹‹የወይራ ተክል የሚገኝበት ተራራ›› ማለት ነው፡፡ ይህ ትልቅ ተራራ (ደብረ ዘይት) ከኢየሩሳሌም ከተማ በስተምሥራቅ አቅጣጫ ይገኛል፡፡ ደብረ ዘይት ተራራ ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የዕለተ ምጽአትን ምልክት ለደቀ መዛሙርቱ (ለሐዋርያት) የገለጸበትና ያስተማረበት ቦታ ነው፡፡ ጌታችን በዚህ በደብረ ዘይት ተራራ ተቀመጦ ‹‹ማንም እንዳያስታችሁ ተዘጋጅታችሁ ኑሩ፡፡ ብዙዎች እኔ ክርስቶስ ነኝ እያሉ በስሜ ይመጣሉ፡፡ እስከ መጨረሻው የጸና እርሱ ይድናል …›› እያለ ደቀ መዛሙርቱን አስተምሯቸዋል፡፡

እነርሱም ስለ ዕለተ ምጽአት ምልክትና የመምጫው ጊዜ መቼ እንደሚኾን ጌታችንን ጠይቀውታል፡፡ እርሱም ቀኑን ከእርሱ ከእግዚአብሔር በስተቀር ማንም እንደማያውቀውና ክርስቲያኖች ከኀጢአት ርቀው በዝግጅት መጠባበቅ እንደሚገባቸው አስረድቷቸዋል፡፡ ልጆች! ዓለም የምታልፍበት ቀን ሲደርስ (በዕለተ ምጽአት) ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመላእከት ዝማሬ፣ በመለከት ድምፅ ታጅቦ በኃይልና በግርማ ከሰማይ ወደ ምድር ይመጣል፡፡

አምላካችን በመጣ ጊዜም በተዋሕዶ ሃይማኖትና በክርስቲያናዊ ምግባር ጸንቶ የተገኘ ክርስቲያን በገነት (መንግሥተ ሰማያት) ለዘለዓለሙ በደስታ ይኖራል፡፡ ያለ ክርስቲያናዊ ምግባር ማለትም በኀጢአት ሥራ የኖረ ሰው ደግሞ ለዘለዓለሙ መከራና ስቃይ ወዳለበት ወደ ሲኦል (ገሃነመ እሳት) ይጣላል፡፡ ስለዚህ አምላካችን ለፍርድ ሲመጣ ለእያንዳንዳችን እንደ ሥራችን ኹኔታ ዋጋ ይሰጠናል ማለት ነው፡፡ የጽድቅ ሥራ ስንሠራ ከኖርን ወደ መንግሥተ ሰማያት (የጻድቃን መኖሪያ) እንገባለን፤ ኀጢአት ስንሠራ ከኖርን ግን ወደ ገሃነመ እሳት (የኀጢአተኞች መኖሪያ) እንጣላለን፡፡

ልጆች! እናንተም በዕለተ ምጽአት ወደ መንግሥተ ሰማያት እንድትገቡ በምድር ስትኖሩ ከክፉ ሥራ ማለትም ከስድብ፣ ከቍጣ፣ ከተንኮል፣ ከትዕቢት እና ከመሳሰለው ኀጢአት ርቃችሁ በእውነት፣ በትሕትና፣ ሰውን በማክበር፣ በፍቅር እና በመሳሰለው የጽድቅ ሥራ ጸንታችሁ ለወላጆቻችሁ እየታዘዛችሁ ኑሩ፡፡ ይህንን ለማድረግ እንድትችሉ ደግሞ ከዘመናዊው ትምህርታችሁ ጎን ለጎን ከወላጆቻችሁ ጋር እየተመካከራችሁ (አስፈቅዳችሁ) መንፈሳዊ ትምህርት መማር፣ ቅዱሳት መጻሕፍትን ማንበብ፣ መንፈሳውያን ፊልሞችን መመልከትና መዝሙራትን ማዳመጥ፣ እንደዚሁም በየጊዜው መቍረብ አለባችሁ እሺ?

በጣም ጥሩ ልጆች! ለዛሬው ከዚህ ላይ ይቆየን፡፡ በሚቀጥለው ዝግጅት ስለሌሎች የዐቢይ ጾም ሳምንታት ትምህርት ይዘንላችሁ እንቀርባለን፡፡ እስከዚያው ድረስ ሰላመ እግዚአብሔር ከኹላችን ጋር ይኹን!

የዓለሙ ፍጻሜ ምልክቱ ምንድን ነው? – ክፍል ሁለት

በአባ ዘሚካኤል ደሬሳ

መጋቢት ፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

 ፬.  የሰው ልጅ እና የክህነት ክብርን፣ እንደዚሁም መንፈሳዊ ባህልን ማቃለል

ቅዱስ ጳውሎስ ከዚህ በታች በተጠቀሰው ትምህርቱ በመጨረሻው ዘመን የሚነሡ ሰዎችን ጠባይ ይነግረናል፡፡

 ‹‹ነገር ግን በመጨረሻው ቀን የሚያስጨንቅ ዘመን እንዲመጣ ይህን እወቅ፡፡ ሰዎች ራሳቸውን የሚወዱ ይኾናሉና፤ ገንዘብን የሚወዱ፣ ትምክህተኞች፣ ትዕቢተኞች፣ ተሳዳቢዎች፣ ለወላጆቻቸው የማይታዘዙ፣ የማያመሰግኑ፣ ቅድስና የሌላቸው፣ ፍቅር የሌላቸው፣ ዕርቅን የማይሰሙ፣ ሐሜተኞች፣ ራሳቸውን የማይገዙ፣ ጨካኞች፣ መልካም የኾነውን የማይወዱ፣ ከዳተኞች ችኩሎች፣ በትዕቢት የተነፉ፣ ከእግዚአብሔር ይልቅ ተድላን የሚወዱ ይኾናሉ፡፡ የአምልኮት መልክ አላቸው፤ ኃይሉን ግን ክደዋል፡፡እነዚህ ደግሞ ራቅ፡፡ ወደ ቤቶች ሾልከው እየገቡ ኃጢአታቸው የተከመረባቸውን፣ በልዩ ልዩ ምኞትንም የሚወሰዱትን፣ ዅልጊዜም እየተማሩ እውነትን ወደ ማወቅ ሊደርሱ ከቶ የማይችሉትን ሞኞችን ሴቶች የሚማርኩ ከእነዚህ ዘንድ ናቸውና። ኢያኔስና ኢያንበሬስም ሙሴን እንደተቃወሙት እንዲሁ እነዚህ ደግሞ አእምሮአቸው የጠፋባቸውስለ እምነትም የተጣሉ ሰዎች ኾነው እውነትን ይቃወማሉ፡፡ ዳሩ ግን የእነዚያ ሞኝነት ደግሞ ግልጥ እንደ ኾነ፤ ሞኝነታቸው ለዅሉ ይገለጣልና ከፊት ይልቅ አይቀናላቸውም፤›› /፪ኛጢሞ. ፫፥፩-፯/፡፡

ይህንን ትምህርት ለማገናዘብ እግዚአብሔርን የማያምነውን ሕዝብ ትተን፣ በመላው ዓለም ዅሉ ካሉ የክርስትና ሃይማኖት አማኞች ተግባር አንጻር ጥቂት ነጥቦችን እንደሚከተለው እንመልት፤

ሀ. መንፈሳዊ ባህልን ማፍረስ

ዅሉም ባይኾኑ አንዳንድ አማኞች ‹‹… ከእግዚአብሔር ይልቅ ተድላን የሚወዱ ይኾናሉ፡፡ የአምልኮት መልክ አላቸውኃይሉን ግን ክደዋል …›› የሚያሰኝ ሕይወት የያዙ እንደ ኾኑ ቅዱስ ጳውሎስ አስረግጦ ነግሮናል፡፡ እንደ አማኝ በቤተ ክርስቲያን የሚገኙ፣ ነገር ግን መንፈሳዊ አምልኮ የማይፈጽሙና የራሳቸውን አሳብ በቤተ ክርስቲያን ላይ ሊጭኑ የሚፈልጉትን ነው ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹የአምልኮት መልክ አላቸው፤ ኃይሉን ግን ክደዋል›› ያላቸው፡፡ የእግዚአብሔር ቤት መታዘዝ፣ መከባበርና ሰላም የነገሠበት ነው፡፡ ነገር ግን በአንዳንድ ቦታ እንደሚስተዋለው በቤተ ክርስቲያን ውስጥ በመንፈሳዊው ባህል የጠነከሩ ብዙዎች እንዳሉ ዅሉ አንዳንድ ሥራ ፈቶች በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ፖለቲካ፣ ዘረኝነት፣ አሉባልታ፣ ወዘተ. የመሳሰሉ እኩያን ተግባራትን በማስፋፋት ቤተ ክርስቲያንን ሲያውኩአት ይስተዋላል፡፡

እነዚህም አይሁድ ቀንተው በቤተ ክርስቲያን ላይ ያደረጉትን ክፉ ሥራ ሲገልጥ፡- ‹‹አንዳንዶቹ ተረድተው ከሚያመልኩም፣ ከግሪክ ሰዎች ብዙ፣ ከከበሩትም ሴቶች ጥቂቶች ያይደሉ ከጳውሎስና ከሲላስ ጋር ተባበሩ።  አይሁድ ግን ቀንተው ከሥራ ፈቶች ክፉ ሰዎችን አመጡ፡፡ ሕዝብንም ሰብስበው ከተማውን አወኩ፤›› በማለት ቅዱስ ሉቃስ እንደ ተናገረላቸው ሰዎች ያሉ ናቸው /ሐዋ. ፲፯፥፭/፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም ከላይ እንደ ጠቀስነው ‹‹ወደ ቤቶች ሾልከው እየገቡ ኃጢአታቸው የተከመረባቸውን በልዩ ልዩ ምኞትንም የሚወሰዱትን ዅልጊዜም እየተማሩ እውነትን ወደ ማወቅ ሊደርሱ ከቶ የማይችሉትን ሞኞችን ሴቶች የሚማርኩ ከእነዚህ ዘንድ ናቸውና›› ይላቸዋል፡፡

ለ. የክህነትን ክብር ማቃለል

ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹… ኢያኔስና ኢያንበሬስም ሙሴን እንደ ተቃወሙት እንዲሁ እነዚህ ደግሞ አእምሮአቸው የጠፋባቸው ስለ እምነትም የተጣሉ ሰዎች ኾነው እውነትን ይቃወማሉ። ዳሩ ግን የእነዚያ ሞኝነት ደግሞ ግልጥ እንደ ሆነ፣ ሞኝነታቸው ለዅሉ ይገለጣልና ከፊት ይልቅ አይቀናላቸውም …›› እንዳለው ዅሉ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሐዋርያት በአንብሮተ እድ የሰጣቸው፤ በትውፊት ከእኛ ላይ የደረሰው፤ የድኅነት መፈጸሚያ የኾነው ሥልጣነ ክህነት ዛሬ ካህናት ነን ከሚሉት ጀምሮ እስከ ምእመናን ድረስ እንደ ኢያኔስና ኢያንበሬስ ባሉ ሰዎች ዘንድ እየተናቀ፣ እየተቃለለ ነው፡፡ ከክህነት ጋር በተያያዘ በቤተ ክርስቲያን ከሚፈጸሙ ስሕተቶች መካከል ጥቂቶቹን ቀጥለን እንጠቅሳለን፤

በቅዱስ ወንጌል፡- ‹‹ከዓመፃም ብዛት የተነሣ የብዙዎች ፍቅር ትቀዘቅዛለች፤›› እንደዚሁም፡- ‹‹በዚያን ዘመን ብዙዎች ይሰናከላሉ፤ እርስበርሳቸውም አሳልፈው ይሰጣጣሉ፡፡ እርስ በርሳቸው ይጣላሉ፤›› ተብሎ እንደ ተነገረው /ማቴ. ፳፬፥፲/፤ ኢያኔስና ኢያንበሬስም ሙሴን እንደ ተቃወሙት እንዲሁ ለዘመናት በአንድነት የኖረችውን የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን በድፍረት የሚከፋፍሉ፤ አሳድጋ፣ አስተምራ፣ ክህነት የሰጠቻቸውን እናታቸውን እስከ ማውገዝ ድረስ የደረሱና በድፍረት ኀጢአት የሚበድሉ አገልጋዮች የሚገኙበት ዘመን ላይ ደርሰናል፡፡ ‹‹ዅ ለንጹሖች ንጹሕ ነው፤ ለርኵሳንና ለማያምኑ ግን ንጹሕ የኾነ ምንም የለም፡፡ ነገር ግን አእምሮአቸውም ሕሊናቸውም ረክሶአል፡፡ እግዚአብሔርን እንዲያውቁ በግልጥ ይናገራሉ፡፡ ዳሩ ግን የሚያስጸይፉና የማይታዘዙ፣ ለበጎ ሥራም ዅሉ የማይበቁ ስለ በሥራቸው ይክዱታል፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ/ቲቶ. ፩፥፲፭/፡፡

ሠለስቱ ምእት በኒቂያ ጉባኤ ‹‹ያለ ኢጲስ ቆጶስ ፈቃድ ቤተ ክርስቲያንን የመሠረተ ከክህነቱ ይሻር›› ብለው ደንግገዋል፡፡ ነገር ግን በተለይ በውጭ አገር እየተለመደ የመጣው ጉዳይ የትኛውንም ኤጲስቆጶስ ሳያስፈቅድ አንድ ካህን፣ ከዚያም አልፎ ዲያቆን ወይም ምእመን እንደ ማንኛውም ድርጅት ቤተ ክርስቲያን ከፈትኩ፤ ቦርድ አቋቋምኩ እያለ በድፍረት ምእመናንን ከሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ውጪ በሚደርግበት ዘመን ላይ ደርሰናል፡፡ በእንደዚህ ዓይነት መንገድ ለተቋቋሙ ‹አብያተ ክርስቲያናት› የሚገለገሉበት ሜሮን፣ ታቦት ከየት ተገኘ? የሚሉ ጥያቄዎች ምላሽ የላቸውም፡፡ ‹‹ብዙዎች ይስታሉ›› እንደ ተባለው በድፈረትና በስሕተት መሠረት ላይ የስሕተትና የድፍረትን ግድግዳ ማቆም፤ የስሕተትና የድፍረት ጣሪያንም ማዋቀር እንደ ሕጋዊ ሥራ ከተቈጠረ ሰነባበተ፡፡

‹‹የጥፋት ርኵሰት በተቀደሰው ሥፍራ ቆሞ ስታዩ አንባቢው ያስተውል›› ተብሎ እንደ ተጻፈው /ማቴ. ፳፬፥፲፭/፣ በየአጥቢያው የሚሰማውን ክፉ ወሬ ስናስተውል የዚህን ትንቢት ተፈጻሚነት እንረዳለን፡፡ የተሐድሶ ሤራ፣ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሚፈጠረው ጭቅጭቅ፣ ሐሜት፣ ሙሰኝነት፣ ዘረኝነት፣ ወዘተ. ምን ይነግሩናል? በአንዳንድ የውጭ አገር ክፍሎችም አብያተ ክርስቲያናት በሰበካ ጉባኤ ሳይኾን ለካህናት ክብር በማይጨነቁ የቦርድ አመራሮች መተዳደር ጀምረዋል፡፡ ይህ አሠራር ለዘመናት ቤተ ክርስቲያን ከኖረችበት አገልግሎት አንጻር ስናየው እጅግ የራቀና የከፋ ነው፡፡ ጌታችን ቤተ ክርስቲያንን የመሠረተው በሥልጣነ ክህነት እንድትተዳደር ሲኾን ይህኛው አሠራር ግን በተቃራኒ የቆመ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ምእመኑን አስተምራ፣ አጥምቃ፣ አሳድጋ እንደገና በተንኮለኞች ሤራ ልጆቹዋን ቀስጠው በእርሷ ላይ እንዲያምጹ ማድረግ የጥፋት ርኵሰት መኾኑን ስንቱ ተረድቶት ይኾን?፡፡ በመወጋገዙ ሒደት ያለው ጉዳትንስ ማን አስተዋለው? እግዚአብሔር ይማረን እንጂ እንደ ሰውኛው ከኾነ መጨረሻው ከባድ ነው፡፡

ከዚህ ዅሉ በደል ለመራቅም ቅዱስ ጳውሎስ፡- ‹‹ማንም ልዩ ትምህርት የሚያስተምር፣ ከጌታችንም ከኢየሱስ ክርስቶስ በኾነው ጤናማ ቃልና እግዚአብሔርን ለመምሰል በሚስማማ ትምህርት የማይጠጋ ቢኾን፣ በትዕቢት ተነፍቶአል፤ አንዳችም አያውቅም፡፡ ነገር ግን ምርመራን በቃልም መዋጋትን እንደ በሽተኛ ይናፍቃል፡፡ ከእነዚህም ቅንዓትና ክርክር፣ ስድብም፣ ክፉ አሳብም፣ እርስበርስ መናደድም ይወጣሉ፡፡ አእምሮአቸውም በጠፋባቸው፣ እውነትንም በተቀሙ፣ እግዚአብሔርን መምሰል ማትረፊያ የሚኾን በመሰላቸው ሰዎች ይገኛሉ። እንደነዚህ ካሉት ራቅ፤›› ሲል ያስተማረንን ትምህርት በተግባር ላይ ማዋል ይጠቅመናል /፩ኛጢሞ. ፮፥፫-፭/፡፡ በእርግጥ ኢያኔስና ኢያንበሬስ ሙሴን ቢቃወሙትም ሙሴ ሥልጣኑ ከእግዚአብሔር የተሰጠው በመኾኑ የእግዚአብሔር ክብር በእርሱ ላይ፤ ቍጣው ደግሞ በበደለኞቹ ኢያኔስና አንበሬስ ላይ እንደ ተገለጠ ዅሉ፣ ዘለዓለማዊዋ ቤተ ክርስቲያናችንም ክህነታዊ ክብርዋ በእግዚአብሔር ዘንድ ክቡር ነውና በአገልጋዮቿ መከፋፈል አትበተንም፤ አትፈርስም፡፡

ሐ. የሰው ልጅ ክብርንና የዕድሜ ደረጃን አለመጠበቅ

ቅዱስ ጳውሎስ በመልእክቱ፡- ‹‹ሰዎች ራሳቸውን የሚወዱ ይኾናሉና፤ ገንዘብን የሚወዱ፣ ትምክህተኞች፣ ትዕቢተኞች፣ ተሳዳቢዎች፣ ለወላጆቻቸው የማይታዘዙ፣ የማያመሰግኑ፣ ቅድስና የሌላቸው፣ ፍቅር የሌላቸው፣ ዕርቅን የማይሰሙ፣ ሐሜተኞች፣ ራሳቸውን የማይገዙ፣ ጨካኞች፣ መልካም የኾነውን የማይወዱ፣ ከዳተኞች፣ ችኩሎች፣ በትዕቢት የተነፉ …›› በማለት የዘረዘረው የሰው ልጅ የዕድሜ፣ የቅደም ተከተል ትሥሥርና ክብር እንዲጠፋ ለሚሠሩ ሰዎች ተስማሚና በቂ ማስረጃ ነው /፩ኛጢሞ. ፫፥፩-፫/፡፡

በአጠቃላይ የምጽአት ምልክቶች ከመንፈሳዊው እስከ ዓለማዊው፣ ከምሁሩ እስካልተማረው፣ ከትልቁ እስከ ትንሹ ድረስ ያገባውም ያላገባውም፤ ካህኑም መነኵሴው ሳይቀር ብዙዎቹ በአንድነት ከቅድስና ርቀው ከጥፋት ርኵሰት፣ ከመከራ ሕይወት፣ ተቋደሽ መኾናቸውን የሚያመላክቱ ናቸው፡፡ ቅዱስ ዳዊት፡- ‹‹ከክብሩ ውበት ከጽዮን እግዚአብሔር ግልጥ ይመጣል።  አምላካችን ይመጣል፤ ዝምም አይልም፡፡ እሳት በፊቱ ይቃጠላል፤ በዙሪያውም ብዙ ዐውሎ አለ፤›› ሲል እንደ ተናገረው /መዝ.፵፱፥፪-፫/፤ ቅዱሳት መጻሕፍትም ተባብረው እንደ መሰከሩት ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በድንገት ይመጣል፤ አይዘገይም፡፡

ከላይ እንደ ተዘረዘረው ከመንፈሳውያን እስከ ዓለማውያን ድረስ ብዙ ሰዎች የተጠመዱበት በዓለማዊ ሥራ ላይ ነው፡፡ ከዚህም በኋላ የበለጠ በሥጋ ሥራ እየተወጠሩ ይሔዳሉ እንጂ ከጥቂቶቹ በስተቀር ወደ መንፈሳዊው የተጋድሎ ሕይወት የሚያዘነብል ሰው (ምእመን) ይኖራል ለማለት ያስቸግራል፡፡ እንዲያውም በዐመፅ እየበረታ በቤተ መቅደሱ ሳይቀር የድፍረት ኀጢአት የሚሠራው እየበዛ ሊመጣ ይችላል፡፡ ከዚህ ዅሉ ኀጢአት ለመራቅና ወደ መንፈሳዊው ተጋድሎ ለመምጣት እግዚአብሔርን ደጅ መጽናት ያስፈልጋል፡፡ ስለዚህም ክርስቲያኖች ነን የምንል ዅሉ የጥፋት ትንቢቱ በእኛ ላይ እንዳይፈጸምብን አሁኑኑ ሳናመነታ ንስሐ መግባትና በትንቢት ከተገለጡት ርኵሰቶች ጨክነን መራቅ ይገባናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር! ወለወላዲቱ ድንግል! ወለመስቀሉ ክቡር!

የዓለሙ ፍጻሜ ምልክቱ ምንድን ነው? – ክፍል አንድ

በአባ ዘሚካኤል ደሬሳ

መጋቢት ፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በዐቢይ ጾም ውስጥ ካሉት ሳምንታት ደብረ ዘይት አምስተኛው ሳምንት ላይ ይውላል፡፡ ደብረ ዘይት ትርጕሙ ‹‹የወይራ ዛፍ፣ ተራራ›› ማለት ሲኾን፣ ይህም በኢየሩሳሌም በሚገኘው በደብረ ዘይት ተራራ ቅዱሳን ሐዋርያት ‹‹የዓለሙ ፍጻሜ ምልክቱ ምንድን ነው?›› /ማቴ.፳፬፥፫/ ብለው ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በጠየቁት ጊዜ እርሱም የማይቀረውን የዓለም ፍጻሜና አስቀድመው የሚፈጸሙ ምልክቶችን አስረድቷቸዋል፡፡

ቤተ ክርስቲያንም ይህንኑ በደብረ ዘይት ሳምንት ታስበዋለች፤ በቅዱሳት መጻሕፍት የተጠቀሱትን የትንቢት ምልክቶች ከተግባራዊ የዓለም ክንዋኔዎች አንጻር በማገናዘብ ለምእመናኑ ታስተምራለች፡፡ በመኾኑም በቤተ ክርስቲያናችን በደብረ ዘይት ሳምንት ምጽአትን የሚመለከቱ ምሥጢራት በሰፊው ይነገራሉ፡፡ በዚህ ዝግጅት በዓለም እየተከሠቱ ያሉ ወቅታዊ ምልክቶችን ከቅዱሳት መጻሕፍት ቃል ጋር በማገናዘብ መጠነኛ ትምህርት ይዘን ቀርበናል፤

የሰው ልጅ ሲፈጠር ጀምሮ ስለ ራሱ መጨረሻና ስለ ዓለም ፍጻሜ ምንነት ማወቅን እንደሚሻ ቅዱሳት መጻሕፍት ያስረዱናል፡፡ ከእነዚህም በተለይ በደብረ ዘይት ዕለት ቤተ ክርስቲያን የምታስተምረው፤ ቅዱሳን ሐዋርያት ‹‹የዓለሙ ፍጻሜ ምልክቱ ምንድን ነው?›› በማለት የጠየቁት ጥያቄ ቅድሚያ ይሰጠዋል፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሐዋርያት ከመለሰላቸው ዋነኛውና ቀዳሚው የምጽአቱ ምልክት የሐሳዊ መሲሕ መምጣት ነው፡፡ ሐሳዊ መሲሕ ማለት በቀጥታ ትርጕሙ ‹‹ሐሰተኛ የኾነበኢየሱስ ክርስቶስ (በአምላክ) ስም የሚመጣ የክርስቶስ ተቃዋሚ›› ማለት ነው፡፡

ትርጕሙን አስፍተን ስንመለከተው ደግሞ ከሃይማኖት ጋር ተያያዥነት ያላቸውም ኾነ የሌላቸው፣ በዓለም ላይ እየተከናወኑ የሚገኙ ጉዳዮችንና የጥፋት መንገዶችን ያጠቃልላል፡፡ የሐሳዊ መሲሕ የጥፋት ሥራዎች በማወቅም ይኹን ባለማወቅ በዓለማውያንና በክፉ መናፍስት ተከታዮች እየተፈለሰፉ ናቸው፡፡ ከእግዚአብሔር የተገኙ የሃይማኖት፣ የሥነ ተፈጥሮ፣ የጋብቻና የመሳሰሉ ድንበሮች ማፍለስን ዓላማ ያደረጉ፤ እንደዚሁም ሰብአዊ ክብር፣ መንፈሳዊና አገራዊ ባህል አገራዊ እንዲጠፋ የሚሠሩ አካላት ዅሉ ከሐሳዊ መሲሕ መደብና ከዓለም ፍጻሜ ምልክት አንጻር የሚታዩ ናቸው፡፡ ጉዳዩን ለማብራራት ያህል የሚከተሉት ነጥቦችን እንመልከት፤

፩. የሃይማኖት ድንበርን ማፍለስ

እግዚአብሔር በመጻሕፍቱ ‹‹አባቶችህ ያኖሩትን (የሠሩትን) የቀድሞውን የድንበር ምልክት አታፋልስ›› /ምሳ.፳፪፥፳፰/ በማለት ያዘዘውን ትምህርት መጣስ ማለትም የሃይማኖት ድንበርን ማፍለስ ከሐሳዊ መሲሕ ተግባር ውስጥ የሚመደብ ነው፡፡ አፈጻጸሙም ሰዎች የእግዚአብሔርን ማንነት እንዳያውቁ ከማድረግ ይጀምራል፡፡ ከዚህም አንዱ ሐሳዊ መሲሕ በእግዚአብሔር ስም በተለያየ ኹኔታና መንገድ መገለጥ ነው፡፡ ‹‹‹እኔ ክርስቶስ ነኝ› እያሉ ብዙ ሰዎች በእኔ ስም ይነሣሉ›› /ማቴ. ፳፬፥፭/፡፡

ይህም እንደ መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትምህርትና የቅዱሳን ሐዋርያት ስብከት መሠረት ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር የባሕርይ ልጁ እንደ ኾነ የማይሰብክ ዅሉ ከሐሳዊ መሲሕ ትምህርት ይመደባል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም በመልእክቱ ‹‹ኢየሱስ ክርስቶስም በሥጋ እንደ መጣ የማይታመን መንፈስ ዅሉ ከእግዚአብሔር አይደለም፤ ይህም የክርስቶስ ተቃዋሚው መንፈስ ነው፡፡ ይህም እንደማመጣ ሰምታችኋል፤ አሁንም እንኳ በዓለም አለ፤›› በማለት በእነዚህ ሐሳውያን ላይ ይመሰክርባቸዋል /፩ኛዮሐ. ፬፥፫/፡፡

በመኾኑም ከዚህ በፊት ያለፉ፣ አምላክ ነን ብለው እንደ ተነሡት ቴዎዳስ ዘግብጽና ይሁዳ ዘገሊላ /ሐዋ. ፭፥፴፮-፴፯/፤ ከዚያም በኋላ በየጊዜው እንደ ተነሡ መናፍቃን በዚህ ዘመንም ‹‹ኢየሱስ ነኝ … ኢየሱስ በእኛ ዘንድ አለ …›› እያሉ የዋሁን ሕዝብ የሚያጭበረብሩ ሐሳውያን መሲሖች መጥተዋል፡፡ ከዚህም ሌላ ክርስቶስን ከአብ የሚያሳንሱ (ሎቱ ስብሐት)፣ ነቢይ ነው ብለው የሚያምኑ፣ በመናፍስት አሠራር የሚጠነቁሉ፣ በማቴሪያሊስት (ቁሳዊነት) ወይም በኢቮሉሽን (በዝግመተ ለውጥ) ትምህርት አምነው አምላክ የለም የሚሉ፣ ወዘተ. ዅሉ የሐሳዊው መሲሕ አካላት ናቸው፡፡

አሁንም ቅዱስ ዮሐንስ በመልእክቱ ‹‹ልጆች ሆይ! መጨረሻው ሰዓት ነው፤ የክርስቶስም ተቃዋሚ ይመጣ ዘንድ እንደ ሰማችሁ አሁን እንኳ ብዙዎች የክርስቶስ ተቃዋሚዎች ተነሥተዋል፡፡ ስለዚህም መጨረሻው ሰዓት እንደ እናውቃለን፤›› ይለናል /፩ኛዮሐ. ፪፥፲፰/፡፡ ከዚህ ቃል የምንረዳው የክርስቶስ ተቃዋሚ መምጣት የምጽአት ጊዜው መቃረብ ምልክት መኾኑን ነው፡፡ በተጨማሪም የምጽአትን መቅረብ ከሚያመለክቱ፣ ከሐሳዊው መሲሕ እና ከእርሱ ጋር ተዛማጅ የኾኑ ወቅታዊ ጉዳዮችን ለመረዳት የሚከተሉትን ትንቢቶች እንመልከት፣

‹‹የአውሬው ምስል ሊናገር እንኳ ለአውሬውም ምስል የማይሰግዱለትን ዅሉ ሊያስገድላቸው፣ ለአውሬው ምስል ትንፋሽ እንዲሰጠው ተሰጠው። ታናናሾችና ታላላቆችም፣ ባለ ጠጋዎችና ድሆችም፣ ጌታዎችና ባሪያዎችም ዅሉ በቀኝ እጃቸው ወይም በግምባራቸው ምልክትን እንዲቀበሉ፤ የአውሬውም ስም ወይም የስሙ ቍጥር ያለው ምልክት የሌለበት ማንም ሊገዛ ወይም ሊሸጥ እንዳይችል ያደርጋል። ጥበብ በዚህ አለ። አእምሮ ያለው የአውሬውን ቍጥር ይቍጠረው፤ ቍጥሩ የሰው ቍጥር ነውና፡፡ ቍጥሩም ስድስት መቶ ስድሳ ስድስት ነው፤›› /ራእ. ፲፫፥፲፮-፲፰/፡፡

ይህ የቅዱስ ዮሐንስ ራእይ ከሚመሠጠርበት ትርጕም ውስጥ አንዲት ቅንጣት ብቻ ከዘመኑ አንጻር ብናይ ‹‹የሚናገር የአውሬው ምስል›› ማለት ለእርሱ ያልተገዙትን ወይም ቁጥሩን ያልያዙትን የሚናገርባቸው፤ ‹‹ምልክቱን ያልተቀበሉትን ሊገዙና ሊሸጡ እንዳይችሉ ያደርግል›› ማለት መኖር፣ መሥራት፣ መሸጥ፣ መለወጥ ወዘተ የሚያግዳቸው ሲል ነው፡፡ ይህም አሁን ባለው የዚህ ዓለም አኗኗር አንጻር ሲታይ ተመሳሳይ ጉዳዮች አሉ፡፡ ለምሳሌ መታወቂያ ወረቀት፣ ፓስፖርት፣ ቪዛ፣ የመኖሪያ ፈቃድ ወዘተ በዓለም አጠቃላይ አሠራር እና ባንድ ሰው የመኖር ማንነት ሚና ላይ ተጽዕኖ የሚያደርጉ ነገሮች ናቸው፡፡ እነዚህ መታወቂያ ወረቀቶች የሌሉት ሰው ካለበት የትም መንቀሳቀስ አይችልም፡፡

ከዚህም በላይ ጉዳዩን ስናሰፋው በሠለጠኑት ዓለማት አሠራር የእያንዳንዱ ሰው የጣት አሻራ በዘመናዊ (ኮምፒውተራይዝድ) መንገድ የተደራጀ በመኾኑ፣ ከዚህ አደረጃጀት ውስጥ ካልተካተተ በቀር ማንም ሰው በዚያች አገር ሊኖር፣ ሊዘዋወር፣ ሊሠራ፣ ሊነግድ ወዘተ. አይችልም፡፡ በዚህ የኮምፒውተር ድር አደረጃጀት ውስጥ ያለ አንድ ሰው ወደየትኛውም ዓለም ቢንቀሳቀስ በጣቱ አሻራ ይታወቃል፡፡ ወንጌላዊው ዮሐንስ በትንቢቱ፡- ‹‹አእምሮ ያለው የአውሬውን ቍጥር ይቍጠረው፤ ቍጥሩ የሰው ቍጥር ነውና፤ ቍጥሩም ስድስት መቶ ስድሳ ስድስት ነው፤››  የሚለውም ይህን ጉዳይ የሚያደራጀው ሌላ አካል ሳይኾን የሰው ልጅ መኾኑን የሚያመለክት ነው፡፡ ‹‹ስድስት መቶ ስድሳ ስድስት›› የሚለው ቍጥር የሰው ልጅ የጅማት ቁጥር ነውና፡፡

ሌላው የምጽአት መቃረብ ምልክት የሐሳዊው መሲሕ ዘመቻን አውቀው በድፍረት፣ ላላወቁት በረቀቀ መንገድ እግዚአብሔርን ያመለኩ አስመስለው የእግዚአብሔርን ስም፣ እመቤታችንን ቅድስት ድንግል ማርያምን፣ በአጠቃላይ ቅዱሳንን መስደብ ነው፡፡ እነዚህ በልዩ ልዩ ዘመናት ሲፈጸሙ የቆዩ ተግባራት ዛሬም ተጠናክረው በመፈጸም ላይ ይገኛሉ፡፡ ሩቅ ሳንሔድ ዛሬ ቤተ ክርስቲያናችንን እየተፈታተነ ያለው የተሐድሶአውያን መናፍቃን ትልቁ ሤራ የእግዚአብሔር ወልድን አምላክነት፤ የድንግል ማርያምን ክብርና አማላጅነት፤ የታቦትንና የመስቀልን ክብር፤ የቅዱሳንን ቅድስና እና አማላጅነት መቃወም ነው፡፡ የተሐድሶ ኑፋቄ እንቅስቃሴ በሥራው የአውሬው መንፈስ አራማጅና መንገድ ጠራጊ መኾኑን ቅዱስ ዮሐንስ በራእዩ እንዲህ በማለት ያረጋግጥልናል፤

‹‹ለዘንዶውም ሰገዱለት፤ ለአውሬው ሥልጣንን ሰጥቶታልና፡፡ ለአውሬውም ‹አውሬውን ማን ይመስለዋል? እርሱንስ ሊዋጋ ማን ይችላል?› እያሉ ሰገዱለ፡፡ ታላቅንም ነገርና ስድብን የሚናገርበት አፍ ተሰጠው፡፡ በዐርባ ሁለት ወርም እንዲሠራ ሥልጣን ተሰጠው፡፡ እግዚአብሔርንም ለመሳደብ ስሙንና ማደሪያውንም በሰማይም የሚያድሩትን ሊሳደብ አፉን ከፈተ። ቅዱሳንንም ይዋጋ ዘንድ ድልም ያደርጋቸው ዘንድ ተሰጠው፡፡ በነገድና በወገንም በቋንቋም በሕዝብም ዅሉ ላይ ሥልጣን ተሰጠው። ከዓለምም ፍጥረት ጀምሮ በታረደው በግ ሕይወት መጽሐፍ ስሞቻቸው ያልተጻፉ በምድር የሚኖሩ ዅሉ ይሰግዱለታል፤›› /ራእ. ፲፫፥፬-፰/፡፡

ሌላኛው በዓለም ላይ የሚታየው በሰዎች ዘንድ ክብርን፣ ዝናንና ታዋቂነትን ለማግኘት ሲባል ራስን ከፍ ማድረግና እንደ አማልክት መቍጠር ከሐሳዊው መሲሕ ጋር ያስመድባል፡፡ በተመሳሳይ መልኩ ሊቀ ነቢያት ሙሴ እንደ ገለጸው የሰናዖር ሰዎችን ኀጢአት ስናስተውል የተነሡበት ዋነኛው ነጥብ ‹‹ስማችንን እናስጠራ›› የሚለው ነበር፡፡ ‹‹‹ኑ! ለእኛ ከተማና ራሱ ወደ ሰማይ የሚደርስ ግንብ እንሥራ፤ በምድር ላይ ሳንበተንም ስማችንን እናስጠራው› አሉ፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ /ዘፍ. ፲፩፥፬/፡፡ በዚህ እኩይ አሳብ ምክንያት ነው እግዚአብሔር ቋንቋቸውን የደባለቀባቸው፡፡ የሰናዖር ሰዎች ያሰቡትና የተመኙት ትውልዱ እግዚአብሔርን ማድነቅ ትቶ፣ ለዘለዓለም ስማቸውን ሲጠራና ሥራቸውን ሲያደንቅ እንዲኖርላቸው ነበር፡፡ ዛሬም ብዙዎቹ ይህንን የሰናዖርን ኀጢአትና የጥፋት ጉዞ እንደ ዓላማ ይዘው በመንቀሳቀስ ላይ ይገኛሉ፡፡

፪. የሥነ ተፈጥሮ ሕግመጣስ

እግዚአብሔር አምላካችን የፈጠረው ፍጥረት ፍጹም በመኾኑ ይህ ቀረህ፤ ይህ ይጨመርልህ የሚባል አይደለም፡፡ ነገር ግን በዚህ ወቅት ሰው ልዩ ልዩ ጥቅማጥቅም ለማግኘት ሲል ዝርያቸው የተለያየ ፍጥረታትን (እንስሳትና ተክሎችን) ማዳቀልንና ማደበላለቅን ተያይዞታል፡፡ በተቃራኒውም የሰውን ቍጥር ለመቀነስ የማያደርገው ሩጫ የለም፡፡ የሰውን ቍጥር ለመቀነስ በሚደረጉ ሕክምናዎች ምክንያትም ሰዎች ለተለያዩ በሽታዎች ተዳርገዋል፡፡ ከዚህም ሌላ በዚህ መሰሉ ድጋፍና ማበረታቻ በተለይ በሠለጠኑ የዓለም ክፍሎች ብዙዎቹ የግብረ ሰዶም ፈጻሚና አስፈጻሚ ኾነዋል፡፡

ይህም አምላክ የሠራውን የፍጥረት ሕግ በማጣጣልና በመጣስ ሰው ላሻሽል ወደሚል ያዘነበለ መኾኑንና የሰውን ልጅ ቅጥ ያጣ ድፍረት ያሳያል፡፡ እግዚአብሔር ግን ሥነ ፍጥረቱን እንዲያደባልቁበት አይፈልግም፡፡ ለዚህም ነው ሊቀ ነቢያት ሙሴን፡- ‹‹ሥርዓቴን ጠብቁ። እንስሳህ ከሌላ ዓይነት ጋር አይደባለቅ፤ በእርሻህም ሁለት ዓይነት ዘር አትዝራ፤›› ሲል ያዘዘው /ዘሌ. ፲፱፥፲፱/፡፡ ግብረ ሰዶምን በተመለከተም ‹‹ማናቸውም ሰው ከሴት ጋር እንደሚተኛ ከወንድ ጋር ቢተኛ ሁለቱ ጸያፍ ነገር አድርገዋል፤ ፈጽመው ይገደሉ፡፡ ደማቸው በላያቸው ነው፤›› ተብሎ ተጽፏል /ዘሌ. ፳፥፲፫/፡፡

፫.  ጋብቻን ማፍረስ (ማፋታት)

አውሬው (አስማንድዮስ የሚባለው ርኵስ መንፈስ) የጋብቻ ጠላት ኾኖ ነግሦአል፡፡ ስለዚህም ተጋቢዎች ፈተናውን መቋቋም አልቻሉምና በአንድ መኖራቸውን ጠልተው ይለያያሉ (ይፋታሉ)፡፡ አስማንድዮስ (ርኵስ መንፈስ) ከጋቻ ይልቅ ግብረ ሰዶምን እያበረታታ በአንዳንድ አገሮች እንደሚታየው ወንድን ከወንድ፣ ሴትን ከሴት ጋር እያቆራኘ በማምለኪያ ሥፍራዎቻቸው ሳይቀር ጋብቻቸውን እስከ መፈጸም አድርሷቸዋል፡፡ ይህንን ኀጢአት በሚመለከትም ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ይላል፤

‹‹ስለዚህ እርስበርሳቸው ሥጋቸውን ሊያዋርዱ እግዚአብሔር በልባቸው ፍትወት ወደ ርኵሰት አሳልፎ ሰጣቸው፤ ይህም የእግዚአብሔርን እውነት በውሸት ስለ ለወጡ በፈጣሪም ፈንታ የተፈጠረውን ስላመለኩና ስላገለገሉ ነው፡፡ እርሱም ለዘላለም የተባረከ ነው፤ አሜን። ስለዚህ እግዚአብሔር ለሚያስነውር ምኞት አሳልፎ ሰጣቸው፡፡ ሴቶቻቸውም ለባሕርያቸው የሚገባውን ሥራ ለባሕርያቸው በማይገባው ለወጡ፡፡ እንዲሁም ወንዶች ደግሞ ለባሕርያቸው የሚገባውን ሴቶችን መገናኘት ትተው እርስ በርሳቸው በፍትወታቸው ተቃጠሉ፡፡ ወንዶችም በወንዶች ነውር አድርገው በስሕተታቸው የሚገባውን ብድራት በራሳቸው ተቀበሉ። እግዚአብሔርን ለማወቅ ባልወደዱት መጠን እግዚአብሔር የማይገባውን ያደርጉ ዘንድ ለማይረባ አእምሮ አሳልፎ ሰጣቸው፡፡ ዓመፃ ዅሉ፣ ግፍ፣ መመኘት፣ ክፋት ሞላባቸው፡፡ ቅናትን፣ ነፍስ መግደልን፣ ክርክርን፣ ተንኰልን፣ ክፉ ጠባይን ተሞሉ፡፡ የሚያሾከሹኩ፣ ሐሜተኞች፣ አምላክን የሚጠሉ፣ የሚያንገላቱ፣ ትዕቢተኞች፣ ትምክህተኞች፣ ክፋትን የሚፈላለጉ፣ ለወላጆቻቸው የማይታዘዙ፣ የማያስተውሉ፣ ውል የሚያፈርሱ፣ ፍቅር የሌላቸው፣ ምሕረት ያጡ ናቸው፡፡ ‹እንደነዚህ ለሚያደርጉት ሞት ይገባቸዋል› የሚለውን የእግዚአብሔርን ሕግ እያወቁ እነዚህን ከሚያደርጉ ጋር ይስማማሉ እንጂ አድራጊዎች ብቻ አይደሉም፤›› /ሮሜ.፩፥፳፬ እስከ ፍጻሜው/፡፡

 ይቆየን

ቅዱስ ፓትርያርኩ አዘንተኞቹን አጽናኑ

6w5a3729

ቅዱስ ፓትርያኩ ከብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት እና ከሌሎችም የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች ጋር ወደ አዘንተኞቹ ድንኳን ሲገቡ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

መጋቢት ፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት በአዲስ አበባ ከተማ በኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ በተለምዶ ‹‹ቆሼ›› እየተባለ በሚጠራው ሥፍራ መጋቢት ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በድንገተኛ አደጋ ከዚህ ዓለም በሞት የተለዩ ምእመናን ቤተሰቦችን በትናንትናው ዕለት መጋቢት ፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በሥፍራው ተገኝተው አጽናኑ፡፡

በደረሰው ድንገተኛ አደጋ ላለፉና ጉዳት ለደረሰባቸው ወገኖች የተሰማቸውን ኀዘን ቅዱስነታቸው ገልጸው በቃለ እግዚአብሔርና በአባታዊ ምክራቸውም አዘንተኞቹን አጽናንተዋል፡፡

ከቅዱስ ፓትርያርኩ ጋር በሥፍራው የተገኙት ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ፣ የደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅ፤ በክልል ትግራይ ደቡባዊ ዞን ማይጨው፣ ደቡባዊ ምሥራቅ ትግራይና ምሥራቃዊ ዞን አዲግራት አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስም እንደዚሁ ለአዘንተኞቹ የማጽናኛ ትምህርት ሰጥተዋል፡፡

ቆሼ ሠፈር

አደጋው የደረሰበት ቦታና አስከሬን የማውጣቱ ሥራ በከፊል

ቋሚ ሲኖዶሱ ከወሰነው የገንዘብ ድጋፍ በተጨማሪ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከትም በአደጋው ምክንያት በጊዜአዊ መጠለያ ለሚገኙ ወገኖች የአንድ መቶ ሺሕ ብር ድጋፍ ማድረጉን ብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ አስታውቀዋል፡፡

በመጨረሻም ቃለ ምዕዳንና ጸሎተ ቡራኬ ከሰጡ በኋላ ቅዱስ ፓትርያርኩ ወደ መንበረ ፓትርያርካቸው ተመልሰዋል፡፡

መጋቢት ፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ቋሚ ሲኖዶስ በአደጋው ላለፉ ምእመናን የተሰማውን ኀዘን መግለጹና ቤታቸው በአደጋው በመፍረሱ ምክንያት በጊዜአዊ መጠለያ ለሚገኙ ወገኖችም ከቤተ ክርስቲያኒቷ የሁለት መቶ ሺሕ ብር ርዳታ እንዲሰጥ መወሰኑ የሚታወስ ነው፡፡

‹‹የአሁኑ እሳት በቍጥጥር ሥር ቢውልም ለወደፊቱ ግን ያሠጋናል … ልጁ ዐረፈ እንጂ ሞተ አይባልም፡፡›› የገዳሙ አበምኔት

ze1

ዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

መጋቢት ፯ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት በሊበን ወረዳ ቤተ ክህነት ዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም አካባቢ (ዙርያ) መጋቢት ፩ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ቀትር ላይ ተነሥቶ የነበረው ከፍተኛ የእሳት ቃጠሎ በቍጥጥር ሥር መዋሉን የገዳሙ አበምኔት መምህር አባ ገብረ ሕይወት አስታወቁ፡፡

ከገዳሙ አባቶች አንዱ አባ ጥላኹን ስዩም እንዳብራሩት እሳቱ የተነሣበት አካባቢ ከገዳሙ በቅርብ ርቀት ላይ የሚገኝ ከመኾኑ ባለፈ ቃጠሎው በከፍተኛ ፍጥነት እየተስፋፋ ስለነበር በአጭር ጊዜ ውስጥ ለመቈጣጠር ባይቻል ኖሮ ከደኑም አልፎ ተርፎ በገዳሙ ላይ ከፍተኛ ጉዳት ያደርስ ነበር፡፡

zuquala

የዝቋላ ገዳም መገኛና የአካባቢው መልክዐ ምድር

የማኅበረ ቅዱሳን አባላትና የልዩ ልዩ ግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች እሳቱን ለማጥፋት በመረባረብ ክርስቲያናዊ ሓላፊነታቸውን የተወጡ ሲኾን፣ በወቅቱ ከገደል ላይ ወድቆ በመጎዳቱ ሕክምና ሲደረግለት የነበረው ኦርቶክሳዊ ወጣት ሸገና ሉሉ (የክርስትና ስሙ ወልደ ዮሐንስ) ከዚህ ዓለም በሞት መለየቱን የአዳማ ማእከል ያደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡ የገዳሙ አበምኔት መምህር አባ ገብረ ሕይወት ‹‹ልጁ ዐረፈ እንጂ ሞተ አይባልም፡፡ ከሰማዕታት እንደ አንዱ የሚቈጠር ነው›› ሲሉ የወልደ ዮሐንስ መጠራት ሰማያዊ ዋጋ የሚያስገኝ ሞት መኾኑን አስረድተዋል፡፡ ‹‹ወቅቱ ሌሊት በመኾኑ፣ በዚያውም ላይ ልጁ የአካባቢውን ተፈጥሮ ባለማወቁ ለኅልፈት ቢዳረግም ሞቱ ግን የሚወደድ እንጂ የሚያስቈጭ አይደለም›› ያሉት ደግሞ አባ ጥላኹን ስዩም ናቸው፡፡ በመጓጓዣ እጦት ምክንያት ማኅበረ መነኮሳቱ በሥርዓተ ቀብሩ ላይ ለመገኘት እንዳልቻሉ ያስታወሱት አበምኔቱ ለወጣቱ በገዳሙ ጸሎተ ፍትሐት እንደተደረገለትና ለወደፊቱም ቤተሰቦቹን ለማጽናናት ኹኔታዎችን እያመቻቹ እንደሚገኙ ጨምረው ገልጸዋል፡፡

%e1%8b%9d2

የእሳት ቃጠሎውን ለማጥፋት የምእመናን ተሳትፎ

አበምኔቱ ለዝግጅት ክፍላችን እንደ ገለጹት በገዳሙ አባቶች፤ በአካባቢው ነዋሪዎችና ከልዩ ልዩ ቦታዎች በመጡ የቤተ ክርስቲያን የቍርጥ ቀን ልጆች፤ እንደዚሁም በኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት፣ አየር ኃይል፤ በኦሮምያ ፖሊስ እና በሊበን ወረዳ ፖሊስ ርብርብ ለገዳሙ ሥጋት የነበረው ይህ ከባድ ቃጠሎ በቍጥጥር ሥር ውሏል፡፡ የበረኃውን ሐሩር፣ የእሳቱን ወላፈን፣ እሾኽና ጋሬጣውን፣ ረኃቡንና ጥሙን ተቋቁመው እሳቱን በማጥፋት ገዳሙን ከጥፋት የታደጉ አካላትን ዅሉ አበምኔቱ በአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ስም አመስግነዋል፡፡

‹‹ገዳማችን በስም የገነነ ነገር ግን በብዙ ችግርና ፈተና ውስጥ ያለ ገዳም ነው፡፡ የአሁኑ እሳት በቍጥጥር ሥር ቢውልም፤ ለወደፊቱ ግን ያሠጋናል፡፡ በየዓመቱ በየካቲትና መጋቢት ወሮች ‹እሳት መቼ ይነሣ ይኾን?› እያልን እንጨነቃለን፡፡ ችግሩን ለማስቀረትና ጋታችንን ለመቀነስ ዘላቂ መፍትሔ ያስፈልገናል፤›› ያሉት አበምኔቱ፣ በመጨረሻም ገዳሙ ያለበትን ችግር ለመፍታትና የእሳት ቃጠሎውንም በዘላቂነት ለመቈጣጠር ያመች ዘንድ በገዳሙ የታቀዱ የገቢ ማስገኛ ተግባራትንና በጅምር የቀረውን የውኃ ጕድጓድ ለመፈጸም መላው ሕዝበ ክርስቲያን ድጋፍ ቢያደርግልን፣ ገዳሙ የቤተ ክርስቲያን ብቻ ሳይኾን የአገርም ሀብት ነውና መንግሥትም መንገድ ቢሠራልን ሲሉ በቤተ ክርስቲያን ስም የርዳታ ጥሪአቸውን ያቀርባሉ፡፡

ziquala

ቃጠሎው በደኑ ላይ ያደረሰው ጉዳት በከፊል

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ዕፀዋቱን ለማገዶና ለልዩ ልዩ አገልግሎት የሚጠቀሙ አካላት በመበራከታቸውና በተደጋጋሚ በደረሰው የእሳት ቃጠሎ በደን የተሸፈነው ግዙፉ የዝቋላ ተራራ በመራቆት ላይ እንደሚገኝ፤ በሰሞኑ ቃጠሎም አብዛኛው የደን ክፍል እንደወደመ ከልዩ ልዩ ምንጮች ለመረዳት ተችሏል፡፡ ታሪካዊው የዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳምም ቍጥቋጦ በሚበዛበት፣ ነፋስ በሚበረታበት፣ በረኃማና ወጣገባ መልክዐ ምድር ላይ የሚገኝ በመኾኑና በሌላም ልዩ ልዩ ምክንያት በተደጋጋሚ በእሳት ተፈትኗል፡፡ ለአብነትም መጋቢት ፰ ቀን ፳፻፬ ዓ.ም በገዳሙ ዙርያ ተነሥቶ በነበረው ከባድ ቃጠሎ በደኑ ላይ ከፍተኛ ጉዳት መድረሱ የሚታወስ ነው፡፡

መጋቢት ፩ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በገዳሙ አካባቢ የተነሣውን እሳት ለማጥፋት ሲሯሯጥ በሞት ለተለየው ወጣት ሸገና ሉሉ (ወልደ ዮሐንስ) ሰማያዊ ዕረፍትን፣ ለቤተሰቦቹም መጽናናትን እየተመኘን የቤተ ክርስቲያችንንና የአገራችንን ሀብት የዝቋላ ገዳምን ህልውና ለማስጠበቅ፣ ገዳሙ ያለበትን ችግር በዘላቂነት ለመፍታትና ደኑንም ወደ ነበረበት ተፈጥሮ ለመመለስ ይቻል ዘንድ የሚመለከተን ዅሉ ብናስበበት መልካም ነው እንላለን፡፡

የኀዘን መግለጫ

img_0005

ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ የቅዱስ ሲኖዶስ ርእሰ መንበር እና ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት

መጋቢት ፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም  

የተወደዳችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች! መጋቢት ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በአዲስ አበባ ከተማ በኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ ልዩ ስሙ ‹‹ቆሼ›› እየተባለ በሚጠራው ሥፍራ በድንገተኛ አደጋ ከዚህ ዓለም በሞት ለተለዩ ወገኖቻችን፣ ዛሬ መጋቢት ፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የተሰጠውን የሐዘን መግለጫ እንደሚከተለው አቅርበነዋል፤

በአዲስ አበባ ከተማ መጋቢት ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ምሽት በወገኖቻችን ላይ የደረሰውን የሞት አደጋ አስመልክቶ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የተሰጠ የዘን መግለጫ፡፡

መጋቢት ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ከምሽቱ ፪ ሰዓት ሲኾን በኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ ልዩ ስሙ ‹‹ቆሼ›› እየተባለ በሚጠራው ስፍራ በሚኖሩ ወገኖቻችን ላይ ድንገተኛ የሞት አደጋ ደርሷል፡፡ በደረሰውም አሳዛኝ አደጋ ከፍተኛ ዘን ተሰምቶናል፡፡

በመኾኑም እግዚአብሔር አምላካችን በደረሰው ኅልፈተ ሕይወት ለተጎዱ ወገኖች ቤተሰቦች መጽናናትን፣ ብርታትን እንዲሰጥልን፤ የሟቾችንም ነፍሳት በመንግሥቱ እንዲቀበልልን በመጸለይ የተሰማንን ዘን እየገለጽን፣ ለእነዚሁ በድንገተኛ አደጋ ለተለዩ ወገኖቻችን ከመጋቢት ፯ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ጀምሮ ለሰባት ቀናት በመላ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናትና ገዳማት ጸሎተ ፍትሐት እንዲደረግላቸው፤ እንዲሁም ቤታቸው በመፍረሱ ምክንያት በመጠለያ ለሚገኙ ወገኖቻችን ከቤተ ክርስቲያችን ብር 200,000.00 (ሁለት መቶ ሺሕ) ርዳታ እንዲሰጥ ቋሚ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡

በክርስቶስ ሰላም

(ክብ ማኅተምና የብፁዕ አቡነ ገሪማ ፊርማ አለው)

አባ ገሪማ ሊቀ ጳጳስ ዶክተር

የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽሕፈት ቤት፣

የውጭ ግንኙነት የበላይ ሓላፊ

‹‹ሰው የለኝም››

በመምህር ኃይለሚካኤል ብርሃኑ

መጋቢት ፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ኃይለ ቃሉን የተናገረው በደዌ ዳኛ ተይዞ የአልጋ ቁራኛ ኾኖ ይኖር የነበረው መጻጕዕ ነው፡፡ መጻጕዕ ማለት በሽተኛ ማለት ነው፡፡ መጻጕዕ ይህንን የኀዘን ሲቃ የተሞላበት ተስፋ የመቁረጥ ምልክት የኾነውን ‹‹ሰው የለኝም›› የሚለውን አቤቱታ ያቀረበው ሳይንቅ ለጠየቀው፣ አይቶ በቸልታ ላላለፈው፣ የሰውን ድካሙን ለሚረዳ ለጌታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡

ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ እንደተረከው በኢየሩሳሌም በበጎች በር አጠገብ በዕብራይስጥ ቋንቋ ‹‹ቤተ ሳይዳ›› የምትባል አንዲት መጠመቂያ ነበረች፡፡ አምስትም መመላለሻ ነበረባት፡፡ ቤተ ሳይዳ ማለት ቤተ ሣህል (የይቅርታ ቤት) ማለት ነው፡፡ አምስት መመላለሻ የሚለውን ትርጓሜ ወንጌል እርከን ወይም መደብ ይለዋል፡፡ በእርከኑ ወይም በመደቡ ብዙ ድውያን ይተኛሉ፡፡ ከእነሱም ውስጥ የታወሩ፣ አንካሾች፣ የሰለሉ፣ ልምሹ የኾኑ፣ የተድበለበሉ በየእርከን እርከኖች ላይ ይተኛሉ፡፡ የእግዚአብሔር መልአክ ውኃውን ለመቀደስ በየዓመቱ በሚወርድ ጊዜ ድምፁ እስኪያስተጋባ ድረስ ውኃው ይናወጣል፡፡ ድውያኑም በዚያ ሥፍራ ተኝተው የውኃውን መናወጥ ይጠባበቃሉ፡፡ ምክንያቱም በዓመት አንድ ጊዜ ብቻ ውኃው ሲናወጥ ቀድሞ ወደ ውኃው የገባ አንድ ሰው ከደዌው ይፈወስ ነበርና፡፡

ፈውሱ በየጊዜው ከዓመት አንድ ጊዜ ይደረግ የነበረው የእግዚአብሔር ተአምራት በአባቶቻችን ጊዜ ነበር እንጂ አሁንማ የለም ብለው ድውያኑ ከማመን እንዳይዘገዩ ሲኾን፣ የድውያኑ መፈወስ አለመደጋገሙም (በዓመት አንድ ጊዜ ብቻ መፈጸሙም) በኦሪት ፍጹም ድኅነት እንዳልተደረገ ለማጠየቅ ነው፡፡ በዚያም ከሠላሳ ስምንት ዓመት ጀምሮ የታመመ አንድ ሰው ነበረ፡፡ ከአልጋው ላይ ተጣብቆ ይኖር ነበር፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ወደዚያ ሰው ቀርቦ አየው፡፡ ጌታችን ክብር ይግባውና ተጨንቀን እያየ ዝም የማይለን፣ ስንቸገርም የሚረዳን ቸር አምላክ ነውና መጻጕዕ በደዌ ዳኛ በአልጋ ቁራኛ ተይዞ ለብዙ ዓመታት እንደተሰቃየ፣ ደዌው እንደጸናበት መከራውም እንደበረታበት አውቆ በርኅራኄ ቃል ‹‹ልትድን ትወዳለህን?›› አለው፡፡ ፈቃዱን መጠየቁ ነው፡፡

አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር ፍትሐዊ ነውና ለማዳን የእያንዳንዳችን ፈቃደኝነት ይጠይቃል እንጂ ሥልጣን ስላለው፣ ክንደ ብርቱና ዅሉን ማድረግ የሚቻለው ስለኾነ ብቻ ያለ ፈቃዳችን የሚገዛን አምላክ አይደለም፡፡ በእኛ ላይ የሚያደርገውን የማዳኑን ሥራ ‹‹ልትነጻ ትወዳለህን፣ ምን እንዳደርግልህስ ትሻለህ?›› በማለት ከጠየቀ በኋላ ‹‹እንደእምነትህ ይኹንልህ፤ እንደእምነትሽ ይኹንልሽ›› እያለ በነጻነት እንድንመለላለስ ነጻነታችን ያወጀልን የፍቅር አምላክ ነው፡፡ መጻጕዕንም ‹‹ልትድን ትወዳለህን?›› ባለው ጊዜ እሱ ግን የሰጠው ምላሽ እጅግ የሚያሳዝን ነበር፡፡ ‹‹ጌታ ሆይ ውኃው በተናወጠ ጊዜ በመጠመቂያው ውስጥ የሚያኖረኝ ‹ሰው የለኝም› ነገር ግን እኔ ስመጣ ሳለሁ ሌላው ቀድሞኝ ይወርዳል›› ብሎ መለሰለት፡፡ መጻጕዕ፣ ሰዎች ባጣ ጊዜ እንደሸሹት፣ በታመመ ጊዜ እንደተጸየፉት፣ ‹‹እንዴት ዋልኽ? እንዴት አደርኽ?›› የሚለው ሰው እንዳጣ፣ ወገን አልባ እንደኾነ እና ተስፋ እንደቆረጠ ለጌታችን ተናገረ፡፡

ጌታችን የልብን የሚያውቅ አምላክ ሲኾን ‹‹ልትድን ትወዳለህን?›› ብሎ የጠየቀበት ምክንያት አላዋቂ ሥጋን እንደተዋሐደ ለማጠየቅ ነው፡፡ አልዓዛር በሞተ ጊዜ ‹‹መቃብሩን አሳዩኝ ወዴት ነው የቀበራችሁት?›› እንዳለው ዅሉ፡፡ መጻጕዕም በምላሹ ‹‹ሰው የለኝም›› ማለቱ ኢየሱስ ክርስቶስን ሲያየው የሠላሳ ዓመት ጎልማሳ ነውና የውኃውን መናወጥ ተጠባብቆ ያወርደኛል ብሎ በማሰቡ ነው፡፡ አንድም አምስት ገበያ ሰው ይከተለው ነበርና አንዱን ሰው ያዝልኛል ብሎ ነው፡፡

ብዙዎቻችን የሕይወታችን ዋልታ በሰው እጅና በሰው ርዳታ ያለ ይመስለናል፡፡ ሰዎች ካልረዱን፣ ካልደጎሙን፣ አይዟችሁ ካላሉን፣ ከጎናችን ካልኾኑና በሰዎች ካልታጀብን ነገር ዅሉ የማይሳካልን ይመስለናል፡፡ ለዚህም ነው በሰዎች ትከሻ ላይ እንወድቅና ክንዳቸውን ተመርኩዘን እነሱ ሲወድቁ አብረን የምንወድቀው፡፡ ሲጠፉም አብረን ለመጥፋት የምንዳረገው፡፡ እስኪ ከሚደክመው ከሰው ትከሻ፣ ከሚዝለው ከሰው ክንድ እንውረድና በማይዝለውና በማይደክመው በአምላክ ክንድ ላይ እንደገፍ፡፡ እርሱ መታመኛ ነው፤ ያሳርፋል፡፡ የማይደክምም ብርቱ መደገፊያ ነው፡፡

መጻጕዕ ዅሉ ነገሩ በሰዎች እጅ ላይ ነው ብሎ ስላሰበና የሰዎች ርዳታ ስለቀረበት ተስፋ ቆርጦ ነበር፡፡ የተማመነባቸው ሰዎችም ሲርቁት ሕይወቱ ጨልሞበት ነበርና ‹‹ሰው የለኝም›› አለ (ዮሐ.፭፥፯)፡፡ የተቸገረውን ለመርዳት፣ ድሃውን ባዕለ ጸጋ ለማድረግ፣ የተጨነቀችቱን ነፍስ ለማጽናናት አማካሪ የማይሻው አምላክ ግን ወዲያውኑ ‹‹ተነሣና አልጋህን ተሸክመህ ሒድ›› አለው፡፡ ሰውዬው (መጻጕዕ) ወዲያውኑ ዳነ፡፡ አልጋውንም ተሸክሞ ሔደ፡፡ ቀነ ቀጠሮ ሳይሰጥ፣ ይህን ያህል ክፈል ሳይል ብቻ መሻቱን ተመልክቶ በአምላካዊ ቃሉ ፈወሰው፡፡

በዮሐንስ ወንጌል ትርጓሜ እንደተገለጸው የእግዚአብሔር መልአክ የቀሳውስት፣ ውኃው የጥምቀት፣ አምስቱ እርከን የአምስቱ አዕማደ ምሥጢር፣ አምስቱ ድውያን የአምስቱ ፆታ ምእመናን ማለትም የአዕሩግ፣ ወራዙት፣ አንስት፣ ካህናት፣ መነኮሳት ምሳሌዎች ናቸው፡፡ እነዚህንም ሰይጣን የሚዋጋበት ለእያንዳንዱ እንደየድካሙ ሊያጠቃው ይሞክራልና ያንን ድል የሚነሱበትን ምሥጢር እንደሚያድላቸው ያጠይቃል፡፡ አዕሩግን በፍቅረ ንዋይ፣ ወራዙትን በዝሙት ጦር፣ አንስትን በትውዝፍት (የምንዝር ጌጥ)፣ ካህናትን በትዕቢት፣ መነኮሳትን በስስት ጦር ሰይጣን ይዋጋቸዋል፡፡ እነርሱም በጥምቀት ባገኙት ኃይል (የልጅነት ሥልጣን) ድል ያደርጉታልና የዚያ ምሳሌ ነው፡፡ ለመጻጕዕ መፈወስ የዘመድ ጋጋታ፣ የሰዎች ርዳታ አላስፈለገውም፡፡ በእግዚአብሔር ቃል ብቻ ተፈውሷል፡፡ ለዚህም ነው ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ ‹‹ችግረኛውን ከቀማኛው እጅ፤ ረዳት የሌለውንም ምስኪን ያድነዋልና፤›› (መዝ.፸፪፥፲፪) ሲል የተቀኘው፡፡ ጻድቁ ኢዮብም እንዲሁ ‹‹ረዳት (ኃይል) የሌለውን ምንኛ ረዳኸው፤›› (ኢዮ.፳፮፥፪) በማለት የእግዚአብሔርን አዳኝነት መስክሯል፡፡

የድንግል ማርያም ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ በሕይወቱ የደረሰለት ሰው እንዲህ ይባረካል፡፡ ስለዚህ ሰው የለኝም፣ ገንዘብ የለኝም፣ ሥልጣን የለኝም፣ ወገን የለኝም፣ ረዳት የለኝም በማለት ተስፋ የቆረጥን ሰዎች እግዚአብሔር ከሰውም፣ ከሥልጣንም፣ ከገንዘብም በላይ ነውና እርሱን ተስፋ አድርገን ዅል ጊዜ በስሙ መጽናናት እና የሚያስጨንቀንን ዅሉ በእርሱ ላይ መጣል እንደሚገባን መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት ‹‹አቤቱ የሚፈልጉህ ዅሉ በአንተ ደስ ይበላቸው፤ ሐሴትም ያድርጉ፡፡ ዅልጊዜ ማዳንህን የሚወዱ ዘወትር እግዚአብሔር ታላቅ ይኹን ይበሉ፤›› (መዝ.፵፥፲፮) እንዳለው ዅሉ ዅል ጊዜም በአምላካችን እግዚአብሔር ደስተኞች እንኹን፡፡

   ወስብሐት ለእግዚአብሔር

የዐቢይ ጾም ሳምንታት (ለሕፃናት) – ክፍል ሁለት  

በልደት አስፋው

መጋቢት ፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች? ባለፈው ዝግጅታችን ከመጀመሪያው እሑድ እስከ ሦስተኛው እሑድ (ከዘወረደ ጀምሮ እስከ ምኵራብ) ድረስ የሚገኙትን የዐቢይ ጾም ሳምንታት የሚመለከት ትምህርት አቅርበንላችሁ ነበር፡፡ ዛሬ ደግሞ አራተኛውን የዐቢይ ጾም ሳምንት (መጻጕዕን) የሚመለከት ትምህርት ይዘንላችሁ ቀርበናል፡፡ መልካም ንባብ!

፬. መጻጕዕ

ልጆች! አራተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ‹‹መጻጕዕ›› ይባላል፡፡ መጻጕዕ ማለት በሽተኛ ማለት ነው፡፡ ይህ ዕለት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሠላሳ ስምንት ዓመታት በበሽታ ተይዞ የነበረውን ሰው የፈወሰበት ዕለት ነው /ዮሐ.፭.፩-፱/፡፡

ልጆች! ቤተሳይዳ የምትባል አንዲት የጠበል መጠመቂያ ሥፍራ ነበረች፡፡ የእግዚአብሔር መልአክ ወደዚያች መጠመቂያ ሥፍራ እየመጣ ውኃውን ከባረከው በኋላ ቀድሞ ገብቶ የተጠመቀ በሽተኛ ካለበት ከማንኛውም ደዌ (በሽታ) ይፈወስ ነበር፡፡ በዚያ ሥፍራ ለሠላሳ ስምንት ዓመታት ከበሽታው ለመፈወስ ብሎ ሲጠባበቅ የነበረ አንድ መጻጕዕ (በሽተኛ) ነበር፡፡ ውኃው በተናወጠ ጊዜ ሌሎች ቀድመው ገብተው እየተፈወሱ ሲሔዱ እሱ ግን ለሰላሣ ስምንት ዓመት በዚያ ቆየ፡፡

ከዚያ በኋላ ጌታችን በዚያ ሥፍራ ሲያልፍ ይህንን መጻጕዕ ተኝቶ አየው፡፡ በዚህ ጊዜ ለብዙ ዘመን እንዲሁ እንደ ነበረ አውቆ ‹‹ልትድን ትወዳለህን?›› ብሎ ከጠየቀው በኋላ እምነቱንና ጽናቱን አይቶ ‹‹ተነሣና አልጋህን ተሸክመህ ሒድ›› አለው፡፡ በጌታችን ቃል ሰውዬው ወዲያውኑ ከበሽታው ዳነ፤ አልጋውንም ተሸክሞ የእግዚአብሔርን ቸርነት እየመሰከረ ሔደ፡፡ በአጠቃላይ አራተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት የመጻጕዕ ታሪክ የሚነገርበት፤ እንደዚሁም የአምላካችን ቸርነቱ፣ ይቅርታው፣ መሐሪነቱ የሚታወስበት ዕለት ነው፡፡

ልጆች! ደብረ ዘይትን የሚመለከት ትምህርት ደግሞ በሌላ ቀን እናቀርብላችኋለን፡፡ ለዛሬው ከዚህ ላይ ይቆየን፡፡ እስከዚያው ድረስ ሰላመ እግዚአብሔር ከዅላችሁ ጋር ይኹን!

በዝቋላ ገዳም አካባቢ የተነሣው የእሳት ሰደድ እየተባባሰ መኾኑ ተነገረ

001

በዝግጅት ክፍሉ

መጋቢት ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት በደብረ ከዋክብት ዝቋላ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም አካባቢ መጋቢት ፩ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ቀትር ላይ የተነሣው ከፍተኛ የእሳት ሰደድ እየተባባሰ መኾኑን የገዳሙ አባቶች ተናገሩ፡፡

እሳቱ የተነሣበት ምክንያት በግልጽ ባይታወቅም ትናንትና ረፋድ ላይ በቅርብ ርቀት ላይ ይጤስ የነበረው አነስተኛ እሳት ቀትር ላይ መባባሱንና እሳቱን ለማጥፋትም የገዳሙ መነኮሳት ከቅዳሴ በኋላ ወደሥፍራው መሔዳቸውን ከገዳሙ አባቶች መካከል አንዱ የኾኑት አባ ጥላኹን ስዩም ዛሬ ረፋድ ላይ ለዝግጅት ክፍላችን በስልክ አስታውቀዋል፡፡

‹‹ዓርብ ረቡዕ›› በሚባለው አካባቢ የነበረውን እሳት ሌሊት ላይ በቍጥጥር ሥር ለማዋል ቢቻልም ‹‹የቅዱሳን ከተማ›› በተባለው ቦታ በኩል በአዱላላ ተክለ ሃይማኖት አካባቢ ያለው ቃጠሎ እየተስፋፋ መምጣቱንና ሰደዱን ለመከላከልም አስቸጋሪ መኾኑን አባ ጥላኹን ተናግረዋል፡፡

እሳቱ ወደ ገዳሙ እንዳይጠጋ የመከላከሉ ሥራ እንደቀጠለ መኾኑን የጠቀሱት አባ ጥላኹን እሳት ለማጥፋት ከደብረ ዘይት ከተማ ወደ ገዳሙ ከሔዱ ምእመናን መካከል አንድ ወንድም ከገደል ላይ ወድቆ እንደተጎዳና በአሁኑ ሰዓትም ሕክምና እየተደረገለት እንደሚገኝ ጨምረው ገልጸዋል፡፡

እንደ አባ ጥላኹን ማብራሪያ የገዳሙ መነኮሳት፤ የደብረ ዘይት እና የአካባቢው ነዋሪዎች፤ እንደዚሁም የፌደራል፣ የክልሉና የወረዳው ፖሊስ ኃይል ከትናንትና ጀምሮ እሳቱን ለማጥፋት ከፍተኛ ርብርብ በማድረግ ላይ ቢገኙም የአካባቢው መልክዐ ምድር በረኃማ፣ ቍጥቋጦ የበዛበትና ነፋስ የሚበረታበት ወጣገባ ቦታ መኾኑ ሰደድ እሳቱን በቍጥጥር ሥር ለማዋል የሚደረገውን ጥረት ከባድ አድርጎታል፡፡

በመጨረሻም ሰደዱ እየተስፋፋ ሔዶ በገዳሙ ላይ ጉዳት ከማድረሱ በፊት እሳቱን ሙሉ ለሙሉ ለማጥፋት እንዲቻል መላው ሕዝበ ክርስቲያን በሚቻላቸው ዓቅም ዅሉ ትብብር ያደርጉ ዘንድ አባ ጥላኹን ስዩም በገዳሙና በመነኮሳቱ ስም ጥሪአቸውን ያስተላልፋሉ፡፡

የዐቢይ ጾም ሳምንታት (ለሕፃናት) – ክፍል አንድ

በልደት አስፋው

የካቲት ፴ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች? ደኅና ናችሁ? እግዚአብሔር ይመስገን!፡፡ ልጆች! በልዩ ልዩ ምክንያት አልችል ብለን ዘግይተናል፡፡ በቅድሚያ በገባነው ቃል መሠረት ወቅቱን ጠብቀን ትምህርቱን ባለማቅረባችን እናንተን ይቅርታ እንጠይቃለን፡፡

ልጆች! የካቲት ፲፩ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ባቀረብንላችሁ ትምህርት ከሰባቱ አጽዋማት መካከል ዐቢይ ጾም አንዱ እንደኾነ፣ ዐቢይ ጾም ማለት ታላቅ ጾም ማለት እንደኾነ፣ ጾሙ ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የጾመው ጾም በመኾኑ ታላቅ እንደተባለ፣ ዕድሜአቸው ሰባት ዓመት ከኾናቸው ሕፃናት ጀምሮ ዅሉም የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አማኞች ዐቢይ ጾምን እና ሌሎችንም አጽዋማት መጾም እንደሚገባቸው፣ እንደዚሁም ስምንቱ የዐቢይ ጾም ሳምንታት (እሑዶች) ስማቸው ማን ማን እንደሚባል ነግረናችሁ ነበር፡፡

ልጆች! ሰባቱ አጽዋማት ማን ማን እንደሚባሉም ጠይቀናችሁ ነበር አይደል? መልሱንስ ጠይቃችሁ ተረዳችሁ? በጣም ጥሩ ልጆች! መልሱን እናስታውሳችሁ፤ ሰባቱ አጽዋማት የሚባሉት፡-

፩. ጾመ ነቢያት

፪. ጾመ ገሃድ (ጋድ)

፫. ጾመ ነነዌ

፬. ዐቢይ ጾም

፭. ጾመ ድኅነት (ረቡዕ እና ዓርብ)

፮. ጾመ ሐዋርያት

፯. ጾመ ፍልሰታ (የእመቤታችን ጾም) ናቸው፡፡

በአሁኑ ሰዓት ዐቢይ ጾምን እየጾምን ነው፡፡ የምንገኘውም ሦስተኛው ሳምንት ላይ ሲኾን ስሙም ‹‹ምኵራብ›› ይባላል፡፡ የሚቀጥለውና አራተኛው ሳምንት ደግሞ ‹‹መጻጕዕ›› ተብሎ ይጠራል፡፡

ልጆች! በዛሬው ዝግጅታችን ከመጀመሪያው እሑድ እስከ ሦስተኛው እሑድ (ከዘወረደ ጀምሮ እስከ ምኵራብ) ድረስ የሚገኙትን የዐቢይ ጾም ሳምንታት የሚመለከት ትምህርት ይዘንላችሁ ቀርበናል፡፡ ትምህርቱን እንድከታተሉት በአክብሮት ጋብዘናችኋል!

፩. ዘወረደ

ልጆች! ከዐቢይ ጾም ሳምንታት መካከል የመጀመሪያው ሳምንት ‹‹ዘወረደ›› ይባላል፡፡ ዘወረደ ማለት ከላይ የመጣ፣ የወረደ ማለት ነው፡፡ ይህም አምላካችን ዓለምን ለማዳን ሲል ሥጋ መልበሱን (ሰው መኾኑን) ያመለክታል፡፡ ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሰማይ ወርዶ፣ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተወልዶ፣ በዮርዳኖስ ወንዝ ተጠምቆ፣ ወንጌልን ለዓለም ካስተማረ በኋላ በፈቃዱ መከራ ተቀብሎ፣ በመስቀል ተሰቅሎ፣ ሞቶ፣ ከሙታን ተነሥቶ ዓለምን አድኗል፡፡ ልጆች! የመጀመሪያው ሳምንት የአምላካችን የማዳን ሥራ በስፋት የሚነገርበት ወቅት በመኾኑ ‹‹ዘወረደ›› ተብሎ ተሰይሟል፡፡

፪. ቅድስት

ሁለተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ‹‹ቅድስት›› ይባላል፡፡ ቅድስት ማለት የተለየች፣ የተመረጠች፣ የከበረች ማለት ነው፡፡ ልጆች! ለምን የተለየች፣ የተመረጠች፣ የከበረች እንደተባለች ታውቃላችሁ? ቅዱስ አምላካችን እግዚአብሔር ዓለምን (ሰውን) ለመቀደስ ሲል ወደ ምድር መምጣቱንና ዐቢይ ጾምን መጾሙን ለማስረዳት ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም የሰንበትን ክብር ለማስገንዘብ ነው፡፡ ሰንበት ቅድስት፣ የተለየች፣ የተመረጠች፣ የከበረች ዕለት ናት፡፡ ስለዚህም ልጆች! ሁለተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ‹‹ቅድስት›› ተብሎ ይጠራል፡፡

፫. ምኵራብ

ልጆች! ሦስተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ደግሞ ‹‹ምኵራብ›› ይባላል፡፡ ምኵራብ ማለት አዳራሽ ማለት ነው፡፡ ምኵራብ ድሮ የነበሩ የእግዚአብሔር ሰዎች መንፈሳዊ ትምህርት ይማሩበት የነበረ  ሥፍራ ነው፡፡ በአንድ ወቅት ይህንን የጸሎት ሥፍራ ሰዎች የንግድ ቦታ አደረጉት፡፡ ይህንን ዓለማዊ ተግባር ሲፈጽሙ የነበሩትን ዅሉ ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹ቤቴ የጸሎት ቤት ይባላል፡፡ እናንተ ግን የወንበዴዎች ዋሻ አደረጋችሁት›› ብሎ ከምኵራብ አስወጣቸው፡፡ ከዚያም ቃለ እግዚአብሔር አስተማራቸው፡፡ ልጆች! የእግዚአብሔር ቤት የጸሎት ቤት እንጂ የንግድ መነገጃ ሥፍራ አለመኾኑን ከዚህ ታሪክ እንማራለን፡፡

ለዛሬው በዚህ ይቆየን፡፡ ቀጣዩን ትምህርት ደግሞ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ በሚቀጥለው ዝግጅት ይዘንላችሁ እንቀርባለን፡፡ እስከዚያው ድረስ ሰላመ እግዚአብሔር ከዅላችን ጋር ይኹን!