ቅዱስ ፓትርያርኩ አዘንተኞቹን አጽናኑ

6w5a3729

ቅዱስ ፓትርያኩ ከብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት እና ከሌሎችም የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች ጋር ወደ አዘንተኞቹ ድንኳን ሲገቡ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

መጋቢት ፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት በአዲስ አበባ ከተማ በኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ በተለምዶ ‹‹ቆሼ›› እየተባለ በሚጠራው ሥፍራ መጋቢት ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በድንገተኛ አደጋ ከዚህ ዓለም በሞት የተለዩ ምእመናን ቤተሰቦችን በትናንትናው ዕለት መጋቢት ፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በሥፍራው ተገኝተው አጽናኑ፡፡

በደረሰው ድንገተኛ አደጋ ላለፉና ጉዳት ለደረሰባቸው ወገኖች የተሰማቸውን ኀዘን ቅዱስነታቸው ገልጸው በቃለ እግዚአብሔርና በአባታዊ ምክራቸውም አዘንተኞቹን አጽናንተዋል፡፡

ከቅዱስ ፓትርያርኩ ጋር በሥፍራው የተገኙት ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ፣ የደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅ፤ በክልል ትግራይ ደቡባዊ ዞን ማይጨው፣ ደቡባዊ ምሥራቅ ትግራይና ምሥራቃዊ ዞን አዲግራት አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስም እንደዚሁ ለአዘንተኞቹ የማጽናኛ ትምህርት ሰጥተዋል፡፡

ቆሼ ሠፈር

አደጋው የደረሰበት ቦታና አስከሬን የማውጣቱ ሥራ በከፊል

ቋሚ ሲኖዶሱ ከወሰነው የገንዘብ ድጋፍ በተጨማሪ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከትም በአደጋው ምክንያት በጊዜአዊ መጠለያ ለሚገኙ ወገኖች የአንድ መቶ ሺሕ ብር ድጋፍ ማድረጉን ብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ አስታውቀዋል፡፡

በመጨረሻም ቃለ ምዕዳንና ጸሎተ ቡራኬ ከሰጡ በኋላ ቅዱስ ፓትርያርኩ ወደ መንበረ ፓትርያርካቸው ተመልሰዋል፡፡

መጋቢት ፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ቋሚ ሲኖዶስ በአደጋው ላለፉ ምእመናን የተሰማውን ኀዘን መግለጹና ቤታቸው በአደጋው በመፍረሱ ምክንያት በጊዜአዊ መጠለያ ለሚገኙ ወገኖችም ከቤተ ክርስቲያኒቷ የሁለት መቶ ሺሕ ብር ርዳታ እንዲሰጥ መወሰኑ የሚታወስ ነው፡፡