የትሩፋት ሥራ በቆጠር ገድራ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

መጋቢት ፳፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

አሁን የምንገኝበት የዐቢይ ጾም ሳምንት ስለ ገብር ኄር (ታማኝ አገልጋይ) እና ገብር ሐካይ (ሰነፍ አገልጋይ) የሚነገርበት ወቅት ነው፡፡ ይኸውም ስለ አገልግሎት ትርፋማነትና ዋጋ የምንማርበት ሳምንት ነው፡፡ በተሰጣቸው መክሊት እጥፍ አትርፈው እንደ ተወደሱት ታማኝ አገልጋዮች እኛ ምእመናንም በሃይማኖት ጸንተን፣ በክርስቲያናዊ ምግባር ጎልምሰን እግዚአብሔር እንደየአቅማችን በሰጠን ልዩ ልዩ ጸጋ ተጠቅመን መንፈሳዊ ትርፍ ካስመዘገብን ከአምላካችን ዘንድ ዋጋ እናገኛለን፡፡ በአንጻሩ በሃይማኖታችን ካልጸናን፣ በክርስቲያዊ ምግባር ካልበረታን፣ ጸጋችንን እንደ ሰነፉ ባርያ ደብቀን መንፈሳዊ ትርፍ ካላስመዘገብን እጣ ፋንታችን ቅጣት ይኾናል፡፡

በምድራዊው ሕይወታችን የተሰጠንን ጸጋ ደብቀን ያለ ምግባር የምንኖር ምእመናን ብዙ የመኾናችንን ያህል፣ ከዚህ በተቃራኒ ደግሞ ከሚበሉት ቈርሰው፣ ከሚጠጡት ቀንሰው፣ ከሚለብሱት ከፍለው ለችግረኞች የሚደርሱ፤ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት መፋጠን የሚሽቀዳደሙ፤ በሚጠፋ ገንዘባቸው የማያልፈውን የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ የሚተጉ በጎ አድራጊ ምእመናንም አይታጡም፡፡ በዛሬው ዝግጅታችን እግዚአብሔር አምላክ በሰጣቸው ልዩ ልዩ ጸጋ ለማትረፍ የተነሡ፣ እንደ ልጅነታቸው ቤተ ክርስቲያን የምትጠብቅባቸውን ክርስቲያናዊ ሓላፊነት ለመወጣት የወሰኑ በጎ አድራጊ ምእመናን በቆጠር ገድራ መካነ ቅዱሳን ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ገዳም በማከናወን ላይ የሚገኙትን አርአያነት ያለው የትሩፋት ሥራ ልናስታውሳችሁ ወደድን፡፡ በመጀመርያም የገዳሙን ታሪክ በአጭሩ እናቀርባለን፤

‹ቆጠር› የሚለው ቃል ቦታውን የመሠረቱት ግለሰብ ስም ሲኾን፣ በጊዜ ሒደት ቃሉ የጎሣ መጠርያ ኾኖ ቀጥሏል፡፡ ‹ገድራ› በአካባቢው ቋንቋ የዛፍ ዓይነትን የሚያመለክት ቃል ነው፡፡ አካባቢው ‹ገድራ› የተሰኘው ዛፍ የሚበዛበት በመኾኑ ቦታው ‹ቆጠር ገድራ› ተብሎ ይጠራል፡፡ አካባቢው በተፈጥሮ ደን የተከበበ ሥፍራ ሲኾን፣ ነዋሪዎቹ ከዚህ ደን ውስጥ ዕፀዋትን እንዳይቆርጡ ቃል ኪዳን ገብተዋል፡፡ ስለዚህም የደኑ ህልውና ተጠብቆ ይኖራል፡፡ የቆጠር ገድራ መካነ ቅዱሳን ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ገዳምም በዚህ ቦታ የተመሠረተ ጥንታዊ ገዳም ነው፡፡ ገዳሙ ከጉራጌ ሀገረ ስብከት መንበረ ጵጵስና ወልቂጤ ከተማ በአምሳ ሁለት ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ይገኛል፡፡

በዳግማዊ ምኒልክ ዘመነ መንግሥት የነበሩ የአካባቢው ምእመናን ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን ሊያስገነቡ ቦታዎችን መርጠው ዕጣ ሲጥሉ ዕጣው በተደጋጋሚ ‹ይነኹራ› ለተባለው ቦታ ወጣ፡፡ በዚያ ሥፍራም በመድኃኔ ዓለም ስም ቤተ ክርስቲያን አነጹ፡፡ ይህ ቤተ ክርስቲያን በዕድሜ ብዛት በመጎዳቱ በየጊዜው ዕድሳት እየተደረገለት እስከዛሬ ቆይቷል፡፡ በአሁኑ ሰዓትም ለበርካታ ሕዝበ ክርስቲያን አገልግሎት በመስጠት ላይ ይገኛል፡፡ በወቅቱ የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ የነበሩት ብፁዕ አቡነ መልከ ጼዴቅ የዚህን ሕንጻ የመሠረት ድንጋይ ለማስቀመጥ በ፳፻፪ ዓ.ም ወደ ቦታው በሔዱ ጊዜ ‹ቆጠር ገድራ› ከሚባለው ደናማ ሥፍራ ሲደርሱ በቦታው በመማረካቸው ከደኑ ውስጥ ገብተው ‹‹ገዳም ገዳም ሸተተኝ፤ ከዚህ ቦታ አልወጣም›› አሉ፡፡ ከጥቂት ሰዓታት ቆይታ በኋላ ጉዟቸውን ቀጥለው ይነኹራ መድኃኔ ዓለም ደርሰው ትምህርተ ወንጌልና ቃለ ቡራኬ ሰጥተው ‹‹ዛሬ ከዚህ ቦታ ላይ የመሠረት ድንጋይ እንዳኖር እግዚአብሔር አልፈቀደልኝም›› ብለው የመሠረት ድንጋዩን ሳያስቀምጡ ወደ አዲስ አበባ ከተማ ተመለሱ፡፡

በሌላ ጊዜ ከሕዝበ ክርስቲያኑ ጋር ውይይት አካሒደው በዕድሳት መልክ በድጋሜ ከሚታነጸው ይነኹራ መድኃኔ ዓለም በተጨማሪ በቆጠር ገድራም በኪዳነ ምሕረት ስም ቤተ ክርስቲያን እንዲታነጽ አዘዙ፡፡ ብፁዕነታቸው ፍጻሜውን ሳያዩ ከዚህ ዓለም ውጣ ውረድ ቢያርፉም በጥቅምት ወር ፳፻፫ ዓ.ም እርሳቸው በመረጡት ቦታ የመሠረት ድንጋይ ተቀምጦ ነሐሴ ፲፮ ቀን ፳፻፬ ዓ.ም የቤተ ክርስቲያኑ ቅዳሴ ቤት ከበረ፡፡ በቆጠር ገድራ በአንድ ወቅት በተደረገ ቁፋሮ ሰባት ጥንታውያን የዋሻ ቤተ መቅደሶች፣ ሦስት የሱባዔ መያዣ ቦታዎችና ልዩ ልዩ ንዋያተ ቅድሳት ተገኝተዋል፡፡ ይህም በዚያ ሥፍራ ቀደም ሲል ቤተ ክርስቲያን ታንጾ እንደ ነበር የሚጠቁም ማስረጃ ነው፡፡ በቁፋሮ የተገኙ ሰባቱ የዋሻ ቤተ መቅደሶችም፡- የደብረ ቢዘን ቤተ መቅደስ፣ ቤተ ጎልጎታ፣ ቤተ መድኅን፣ ቤተ ጠበብት፣ ቤተ ኤፍራታ፣ ቤተ ደብረ ብርሃን እና ቤተ ደናግል ይባላሉ፡፡

ከእነዚህ ቤተ መቅደሶች መካከል በቤተ ጎልጎታ የኦሪት መሥዋዕት ይቀርብበት እንደ ነበረ፤ በውስጡም ከወርቅ የተሠራ መሠዊያ እንደ ተገኘና ይህን መሠዊያም በስድስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን በሥፍራው ሲያገለግሉ የነበሩ አባ ማትያስ የተባሉ አባት እንዳይዘረፍ ብለው ቆፈረው እንደ ቀበሩት የአካባቢውን ታሪክ የሚያውቁ አባቶች ይናገራሉ፡፡ የቦታው ታሪክና የንዋያተ ቅድሳቱ ዝርዝርም በቁፋሮው በወጣው ‹ዝንቱ መጽሐፍ ዘአቡነ ማትያስ› በተባለው የብራና መጽሐፍ ተመዝግቦ ይገኛል፡፡ በቁፋሮ የወጡት የወርቅ መሠዊያ፣ የብራና መጻሕፍት፣ ቅዱሳት ሥዕላት፣ እርፈ መስቀል እና ሌሎች ጥንታውያን ንዋያተ ቅድሳት ቤተ መዘክር እስከሚሠራላቸው ድረስ እንዳይጠፉ በምሥጢር እንዲጠበቁ ተደርገዋል፡፡ በዚህ ሥፍራ ከአሁን በፊት ያልወጡና ወደ ፊት በቁፋሮ የሚገኙ ንዋያተ ቅድሳት እንዳሉም ይታመናል፡፡ ከዚሁ ዅሉ ጋርም በገዳሙ የፈለቁት፣ በአምስት ቅዱሳን ማለትም በኪዳነ ምሕረት፣ መጥምቀ መለኮት ዮሐንስ፣ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ እና አባ ማትያስ ስም የተሰየሙት ጠበሎች ለበርካታ ሕሙማን ፈውስ እየሰጡ ተአምራትን እያሳዩ ነው፡፡ በቍጥር ወደ ፳፪ የሚደርሱ የሌላ እምነት ተከታዮችም በገዳሙ ጠበሎች ከሕመማቸው ተፈውሰው፣ የክርስትና ጥምቀትን ተጠምቀው የሥላሴን ልጅነት አግኝተዋል፡፡

ምንጭ፡

  • የማኅበረ ቅዱሳን ኅትመትና ኤሌክትሮኒክስ ሚድያ ዋና ክፍል፤
  • የገዳሙ ሕንጻ አሠሪ ኰሚቴ ያሳተመው በራሪ ወረቀት፤
  • የጉራጌ ዞን ባህል ቱሪዝም እና መንግሥት ኮሚኒኬሽን፡፡
img_0748

መርሐ ግብሩ በጸሎተ ወንጌል ሲከፈት

የዚህ ዅሉ ታሪክ ባለቤት ለኾነችው ቆጠር ገድራ መካነ ቅዱሳን ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ገዳም ደረጃውን የጠበቀ ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን፣ የአብነት ት/ቤት፣ የካህናት ማሠልጠኛ ተቋም እና ቤተ መዘክር ለመሥራት እግዚአብሔር ያስነሣቸው የአካባቢው ተወላጆች ከሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ፈቃድ አግኝተው በመፋጠን ላይ ይገኛሉ፡፡ እነዚህ በጎ አድራጊ ምእመናን ከሀገረ ስብከቱና ወረዳ ቤተ ክህነቱ ጋር በመተባበር ገዳሙን የትምህርትና የልማት ማእከል ለማድረግ እንቅስቃሴ ላይ ናቸው፡፡ የገዳሙን ታሪክ ለትውልድ ለማስተላለፍ ያመች ዘንድ ሰባክያነ ወንጌልንና አስጐብኚዎችን ለመመደብም ታቅዷል፡፡

003

በአጠቃላይ ገዳሙን ወደ ጥንት ስሙና ታሪኩ ለመመለስ የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡ በዚህ መልካም የትሩፋት ሥራም የሕንጻዎቹን ዲዛይን በነጻ በመሥራትና ኰሚቴውን በማስተባበር፣ እንደዚሁም ዓላማውን በማስተዋወቅ ማኅበረ ቅዱሳን ድጋፍ በማድረግ ላይ ሲኾን፣ ማኅበረ ጽዮንም ሌላው አጋር አካል ነው፡፡ ለዚህ መልካም ተግባር የተቋቋመው ሕንጻ አሠሪ ኰሚቴም ለታቀዱት ዘርፈ ብዙ የልማት ሥራዎች ገቢ በማሰባሰብ መንፈሳዊ ተልእኮውን በአግባቡ እየተወጣ ነው፡፡ ኰሚቴው ካከናወናቸው የግንዛቤ ማስጨበጫ እና የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብራት መካከልም የካቲት ፳፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ቦሌ አየር ማረፊያ አካባቢ በሚገኘው ዮድ አቢሲንያ የባህል ምግብ አምባሳደር ያደረገው ልዩ መርሐ ግብር አንዱ ነው፡፡

img_0795

የመርሐ ግብሩ ታዳሚዎች በከፊል

በጸሎተ ወንጌል በተከፈተው በዚህ መርሐ ግብር በካህኑ የተነበበው፣ በዓለ ደብረ ታቦርን የሚመለከተው፣ ‹‹… ሦስት ዳስ እንሥራ …›› የሚለው ኃይለ ቃል የሚገኝበት የወንጌል ክፍል ከገዳሙ የልማት ሥራ ጋር የሚተባበር ምሥጢር አለው (ማቴ. ፲፯፥፩-፬)፡፡

img_0809

መምህር አባ ኤልሳዕ ከደቀ መዛሙርታቸው ጋር ኾነው የአብነት ሥርዓተ ትምህርትን በተግባር ሲያሳዩ

በዕለቱ የገዳሙ አስተዳዳሪ መምህር አባ ኤልሳዕ ከደቀ መዛሙርታቸው ጋር ተገኝተው ንባብ፣ ዜማ፣ ቅኔ፣ የመጻሕፍት ትርጓሜ እና የአቋቋም ሥርዓተ ትምህርትን ለመርሐ ግብሩ ታዳሚዎች በተግባር አሳይተዋል፡፡

img_0757

ዲያቆን ብርሃኑ አድማስ ትምህርተ ወንጌል ሲሰጡ

ዲ/ን ብርሃኑ አድማስም ‹‹የመስጠትና የመቀበል ስሌት›› (ፊልጵ. ፬፥፲-፳) በሚል ኃይለ ቃል ገንዘብንም ኾነ ሌላ ንብረትን ለመንፈሳዊ ዓላማ ማዋል ከእግዚአብሔር ዘንድ የሚያሰጠውን ልዩ ጸጋና የሚያስገኘውን ጥቅም ቅዱሳት መጻሕፍትን ዋቢ በማድረግ አስተምረዋል፡፡

ቀሲስ ምንዳዬ ብርሃኑ እና መጋቤ ስብሐት ዓለሙ አጋ ደግሞ መዝሙር አቅርበዋል፡፡

img_0753

ቀሲስ ምንዳዬ ብርሃኑ መዝሙር ሲያቀርቡ

img_0779

መጋቤ ስብሐት ዓለሙ አጋ በገና ሲደረድሩ

የመርሐ ግብሩ መሪ ዲ/ን ደረጀ ግርማ በበኩላቸው በበጎ አድራጊ ምእመናን የተጀመረው ይህ ገዳሙን የማሳደግ ሥራ ዓላማው በየጊዜው እየቀዘቀዘ የመጣውን የአብነት ትምህርት ለማስፋፋት፣ ጥንታውያን ቅርሶችን በመጠበቅ ለትውልድ ለማስተላለፍ፣ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን አገልግሎት ለማሳደግ እና ስብከተ ወንጌልን በስፋት ለማዳረስ መኾኑን አስገንዝበዋል፡፡

img_0815

የሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ ዲዛይን ተመርቆ ሲከፈት

የገዳሙን ታሪክ የሚያስቃኝ ዘጋቢ ፊልምም ሌላው የመርሐ ግብሩ አካል የነበረ ሲኾን የኰሚቴው ሰብሳቢ እና የዮድ አቢሲንያ የባህል ምግብ አምባሳደር ባለቤት አቶ ትእዛዙ ኮሬ ‹‹የሰማይ አምላክ ያከናውንልናል፤ እኛ በርያዎቹም ተነሥተን እንሠራለን›› በሚል ርእስ በዘገባ መልክ የኰሚቴውን እንቅስቃሴ ለጉባኤው አስረድተዋል፡፡ በዚህ መርሐ ግብር በገዳሙ ሊሠራ የታቀደው ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን፣ ዘመናዊ የአብነት ት/ት ቤት እና የቤተ መዘክር ዲዛይን በአባቶች ቡራኬ ተመርቋል፡፡ በመርሐ ግብሩ የታደሙ ምእመናንም ለዚህ መልካም ሥራ በመሽቀዳደም የሚችሉትን ዅሉ ለማድረግ ቃል ከመግባታቸው ባለፈ በዕለቱ በሚሊዮን የሚቈጠር ገንዘብ ገቢ አድርገዋል፡፡ የሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ ዲዛይን በከፍተኛ መንፈሳዊ ፉክክር በአንድ መቶ ሃያ ሺሕ ብር ጨረታ መሸጡም ብዙዎችን አስደንቋል፡፡ ይህም ሕዝበ ክርስቲያኑ ገንዘቡን ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ለማዋል ያለውን ቍርጠኝነት ያሳያል፡፡

001-copy

ይህን የትሩፋት ሥራ በመደገፍና በማስተባበር የተሳተፉ አካላትን ዅሉ የኰሚቴው ሰብሳቢ አቶ ትእዛዙ ኮሬ በእግዚአብሔር ስም አመስግነው የአካባቢው ተወላጆች ሥራውን ቢጀምሩትም ሓላፊነቱ ግን ለዅላችንም ነውና እያንዳንዱ ምእመን እግዚአብሔር ከሰጠው ገንዘብ ላይ ዐሥራት በማውጣት የገዳሙን ልማት መደገፍ እንደሚገባው አሳስበዋል፡፡ በመቀጠል በዕለቱ የተሰበሰበውን ገንዘብ ያበረከቱ ምእመናንን ሰብሳቢው ካመሰገኑ በኋላ ይህ ገቢ ለታቀደው ልዩ ልዩ ተግባር በቂ ስለማይኾን መላው ሕዝበ ክርስቲያን በያሉበት ርብርብ እንዲያደርጉና የገዳሙን ልማት በጋራ እንዲደግፉ በኰሚቴው አባላት ስም ጥሪ አቅርበዋል፡፡ መርሐ ግብሩም በአባቶች ጸሎት ተፈጽሟል፡፡

img_0774

አቶ ትእዛዙ ኮሬ የኰሚቴውን የሥራ እንቅስቃሴ ሪፖርት ሲያደርጉ

በቆጠር ገድራ መካነ ቅዱሳን ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ገዳም ሊሠራ የታቀደውን መንፈሳዊ ተግባር በገንዘብ፣ በጉልበት፣ በቁሳቁስ ወይም በሐሳብ ለመደገፍ የምትፈልጉ ምእመናን በስልክ ቍጥር፡- 09 11 72 27 93 ወይም 09 21 06 23 82 በመደወል ተጨማሪ መረጃ መጠየቅና ድጋፍ ማድረግ የምትችሉ መኾኑን ኰሜቴው ያሳስባል፡፡ እኛም እንደ ዝግጅት ክፍል የኰሜቴው ሥራና የምእመናኑ ተሳትፎ አርአያነት ያለው፣ ሊበረታታ የሚገባው ተግባር በመኾኑ ይህን መንፈሳዊ እንቅስቃሴ በዚህ መልኩ አስታወስናችሁ፡፡ በመጨረሻም ይህን የትሩፋት ሥራ በመደገፍ የሚጠበቅብንን የልጅነት ድርሻ እንወጣ በማለት መልእክታችንን እናስተላልፋለን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

በበልበሊት ኢየሱስ ገዳም ዙርያ የተነሣው የእሳት ቃጠሎ ጠፋ

የምዕራፈ ቅዱሳን በልበሊት ኢየሱስ ገዳም ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን

በዝግጅት ክፍሉ

መጋቢት ፲፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት በእንሳሮ ወረዳ ቤተ ክህነት በምዕራፈ ቅዱሳን በልበሊት ኢየሱስ አንድነት ገዳም ዙርያ የተነሣው የእሳት ቃጠሎ መጥፋቱን የገዳሙ አበምኔት ገለጹ፡፡

መጋቢት ፲፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ከምሽቱ ፲፩ ሰዓት ገደማ በግልጽ ባልታወቀ ምክንያት የተነሣው ይህ የእሳት ቃጠሎ በገዳሙ መነኮሳት፣ በአካባቢው ሕዝበ ክርስቲያን እና በወረዳው የመንግሥት አካላት ጥረት ከሌሊቱ ፭ ሰዓት ገደማ ጠፍቷል፡፡

01

የአካባቢው መልክዐ ምድር

ቃጠሎው በቤተ ክርስቲያኑ ላይ ምንም ዓይነት ጉዳት ባያደርስም በግምት አምስት ሄክታር የደን ሽፋንና ሦስት ሄክታር የአትክልት ቦታ በድምሩ ስምንት ሄክታር የሚኾነውን የገዳሙ መነኮሳት ያለሙትን የገዳሙን ይዞታ ማውደሙን የገዳሙ አበምኔት በኵረ ትጉሃን ቆሞስ አባ ሐረገ ወይን አድማሱ አስታውቀዋል፡፡

ከሥፍራው ያገኘነው መረጃ እንደሚያመለክተው የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ፣ በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል አገልጋዮች መጋቢት ፲፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በገዳሙ ተገኝተው ማኅበረ መነኮሳቱን ያጽናኑ ሲኾን፣ ማኅበረ መነኮሳቱም ተረጋግተው ወደ ቀደመ የጸሎት ተግባራቸው ተመልሰዋል፡፡

?

ገዳሙ ከሁለት መቶ አምሳ በላይ መነኮሳት እና መነኮሳይያት፤ እንደዚሁም ወደ ሁለት መቶ የሚደርሱ የቅኔ፣ የድጓ እና የቅዳሴ ደቀ መዛሙርት የሚገኙበት ሲኾን፣ ገዳሙ የሚተዳደርበት በቂ ገቢ የሌለው ከመኾኑ ባሻገር የአብነት ተማሪዎቹም በመጠለያ እና በምግብ እጥረት ምክንያት ትምህርታቸውን በአግባቡ ለመከታተል ተቸግረዋል፡፡ ‹‹ስለዚህም የገዳሙን ህልውና ለመጠበቅ እና የአብነት ተማሪዎችን ከስደት ለመታደግ መላው ሕዝበ ክርስቲያን ድጋፋችሁ አይለየን›› ሲሉ የገዳሙ አበምኔት በገዳሙና በማኅበረ መነኮሳቱ ስም ጥሪያቸውን አቅርበዋል፡፡

02

ቃጠሎው ያደረሰው ጉዳት በከፊል

ምዕራፈ ቅዱሳን በልበሊት ኢየሱስ አንድነት ገዳም መልክዐ ምድራዊ አቀማመጡ ለጎርፍ አደጋ ተጋላጭ በመኾኑ በየጊዜው በግምት ስድሳ ሄክታር የሚደርስ የገዳሙ ይዞታ በጎርፍ መወሰዱን፤ በአሁኑ ሰዓትም በክልሉ መንግሥት በጀት በገዳሙ ዙርያ የአፈር ጥበቃ ሥራ እየተከናወነ መኾኑን ከገዳሙ ጽ/ቤት ለመረዳት ተችሏል፡፡

መረጃውን ያደረሰን በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ነው፡፡

የተወደዳችሁ ምእመናን! በየጊዜው በገዳሞቻችን ላይ የሚደርሰውን የእሳት ቃጠሎ እና መሰል አደጋ ከፍተኛ ጉዳት ከማድረሱ በፊት ዅላችንም ተግተን፣ ነቅተን ቤተ ክርስቲያናችንን እንጠብቅ ስንል መልእክታችንን እናስተላልፋለን፡፡

እርማት

በዚህ ዜና ሦስተኛው አንቀጽ ላይ ‹… ስምንት ሺሕ ሄክታር …› በሚል የተገለጸው በስሕተት ስለ ኾነ ስምንት ሄክታር› ተብሎ መስተካከሉን ከይቅርታ ጋር ለማስገንዘብ እንወዳለን፡፡

ክርስቲያናዊ ምግባርን ከገብር ኄር እንማር

በዲያቆን አባተ አሰፋ

መጋቢት ፲፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ታላቁን የጌታችንን ጾም ከጀመርን ስድስተኛው ሳምንት ላይ ደርሰናል፡፡ ይህን ሳምንት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ‹ገብር ኄር› የሚል ስያሜ ሰጥታዋለች፡፡ ትርጕሙም ‹በጎ አገልጋይ› ማለት ሲኾን የስያሜውን መነሻ የምናገኘው በዕለቱ ሥርዓተ ቅዳሴ ከሚነበበው የወንጌል ክፍል ነው (ማቴ.፳፭፥፲፬-፴)፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምሳሌ መስሎ ካስተማራቸው ትምህርቶች መካከል አንዱ የኾነው ይህ የወንጌል ክፍል በርካታ መልእክትታን በውስጡ ይዟል፡፡ በቤተ ክርስቲያን በልዩ ልዩ ሓላፊነት ላይ የሚገኙ ሰዎች ትኩረት ሰጡባቸው የሚገቡ ነጥቦችን ይጠቁማል፡፡ ይህን ለመረዳት ያመቸን ዘንድ ከታሪኩ የመጀመርያ ክፍል በመነሣት ዋና ዋና ነጥቦችን መመርመር ጠቃሚ ነው፤

በዚህ ምሳሌያዊው ታሪክ አንድ ጌታ አገልጋዮቹን ጠርቶ ለእያንዳንዳቸው እንደ ችሎታቸው መጠን ለአንዱ አምስት ለአንዱ ሁለት እንዲሁም ለሌላኛው አንድ መክሊት ነግደው ያተርፉበት ዘንድ እንደ ሰጣቸው ተጠቅሷል፡፡ ከታሪኩ እንደምንረዳው የአገልጋዮቹ ጌታ ለመንገድ ቢዘጋጅም ሀብቱ ግን በተዘጋ ቤት ውስጥ ተቆልፎበት እንዲቀመጥ አልፈለገም፡፡ እንዲያተርፉበት ገንዘቡን ለአገልጋዮቹ ሰጥቷቸዋል፡፡ ሰውዬው ማትረፍ በመፈለጉ ብቻም ገንዘቡን ያለ አግባብ አልበተነም፡፡ ለእርሱ ቀረቤታ የነበራቸውን አገልጋዮቹን ጠርቶ እንደየችሎታቸው መጠን እንዲሠሩበት አከፋፈላቸው እንጂ፡፡

ይህ ጌታ ቅንነትና ርኅራኄ የበዛለት እንደ ኾነ የሚያመላክተን ነገር አለ፡፡ ይኸውም ለአገልጋዮቹ ሓላፊነትን ቢሰጥም እንኳን ከእነርሱ ጋር በነበረው ቀረቤታ ማን ምን መሥራት ይችላል የሚለውን ከግምት ውስጥ በማስገባት ለእያንዳንዳቸው እንደ ሓላፊነት የመሸከም አቅማቸው አምስት፣ ሁለት፣ አንድ እያደረገ መስጠቱ ነው፡፡ የዚህ ጌታ መክሊት አሰጣጥ አድልዎ ያለበት ሊመስለን ይችላል፡፡ ታሪኩን እስከ መጨረሻው ብንከታተለው ግን የባለ መክሊቱን ቅንነት እናስተውላለን፡፡

ይህ ጌታ ለአገልጋዮቹ አትርፉበት ብሎ መክሊቱን ሰጥቷቸው በሔደበት አገር አልቀረም፡፡ ይልቁንም እያንዳንዱ በተሰጣቸው መክሊት ምን እንደ ሠሩበት ሊቆጣጠራቸው ተመልሷል፡፡ ስለዚህ አገልጋዮቹ በሰጣቸው መክሊት ምን እንደ ሠሩ እንደሚጠይቃቸው እያወቀ ከአቅማቸው በላይ የኾነ መክሊትን በመስጠት እንዲጨነቁ አልፈለገም፡፡ በተቃራኒው የምናስተውለው ከአእምሯቸው በላይ ሳይኾን ባላቸው ኃይል ተጠቅመው መሥራትና ማትረፍ የሚችሉትን ያህል መክሊት እንደ ሰጣቸው ነው፡፡

ከብዙ ጊዜም በኋላ የእነዚያ አገልጋዮች ጌታ ሊቆጣጠራቸው ሲመጣ አምስት መክሊት ተቀብሎ የነበረው ሌላ አምስት፣ እንደዚሁም ሁለት መክሊት ተቀብሎ የነበረው ሌላ ሁለት መክሊት አትርፈው ከጌታቸው ፊት እንደ ቆሙ፤ ያ ጌታም በእነዚህ አገልጋዮቹ ታማኝነት ተደስቶ ወደ ደስታ ቦታ እንዳስገባቸው እናያለን፡፡ በተቃራኒው ደግሞ ያ አንድ መክሊት ተቀብሎ የነበረው አገልጋይ ያተርፍባት ዘንድ የተሰጠችውን መክሊት ምድርን ቆፍሮ እንደ ቀበረ፤ ከዚህም አልፎ ‹‹ምን አደረግህባት?›› ተብሎ ሲጠየቅ የዐመፅ ንግግር እንደ ተናገረ፤ በዚህ ያዘነው ጌታውም ያን ክፉ አገልጋይ እንዲቀጣ እንዳደረገው እንረዳለን፡፡ በዚህኛው ክፍል ከተጠቀሰው ታሪክ ሦስቱን አካላት ማለት የመክሊቱን ሰጪ ጌታ፣ በጎ የተባሉ አገልጋዮችን፣ ክፉ እና ሰነፍ የተባለውን አገልጋይ በተናጠል እንመልከታቸው፤

የአገልጋዮቹ ጌታ

ይህ ሰው ለገንዘቡ ጠንቃቃ ከመኾኑ ባሻገር በአገልጋዮቹ ላይ ሙሉ ሥልጣን አለው፡፡ ባለ መታዘዙ ምክንያት በክፉው አገልጋይ ላይ የፈረደበትን ፍርድ (ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ወዳለበት፣ በውጪ ወዳለ ጨለማ አውጡት የሚለው) የጌታው ሙሉ ሥልጣን ያሳያል፡፡ ይህ ጌታ ፍርዱ በእውነት ላይ የተመረኮዘ መኾኑንም በተሰጣቸው መክሊት ላተረፉት ሁለቱ አገልጋዮቹ ከሰጣቸውን ክብር መረዳት ይቻላል፡፡

በጎ እና ታማኝ አገልጋዮች

በአገልጋዮቹ ጌታ በጎ አገልጋዮች የተባሉት አምስት መክሊት የተቀበለውና ሁለት መክሊት የተቀበለው ናቸው፡፡ እነዚህ አገልጋዮች በጎ ለመባል ያበቃቸው አስቀድመው ብዙ ቍጥር ያለው መክሊት በመቀበላቸው አይደለም፡፡ ጉዳዩ የመክሊቱ ብዛት ሳይኾን በተሰጣቸው መክሊት መጠን የሚገባቸውን ያህል ደክመው ማትረፍ መቻላቸው ነው፡፡

ክፉና ሰነፍ አገልጋይ

አንድ መክሊት የተቀበለውን አገልጋይ ከሁለቱ አገልጋዮች ያሳነሰውም ከአንድ በላይ መክሊት አለመቀበሉ ሳይኾን በዚያችው በአንዷ መክሊት እንኳን መሥራት አለመቻሉ ነው፡፡ በአጠቃላይ ይህ አገልጋይ ሦስት መሠረታዊ ስሕተት ፈጽሟል፤

የጌታውን ትእዛዝ በቸልተኝነት መመልከቱ የመጀመርያው ስሕተቱ ነው፡፡ ጌታው ለእያንዳንዳቸው እንደ ችሎታቸው ገንዘቡን ሲሰጣቸው አትርፈው እንዲቆዩት ነው፡፡ እንደ አቅማቸው መስጠቱም አቅማቸው በሚፈቅደው የሥራ ደረጃ እንዲሰማሩ በማሰብ ነበር፡፡ ይህ ሰነፍ አገልጋይ ግን ያደረገው ከታዘዘበት ዓላማ በተቃራኒው መልኩ ነው፡፡ ሊሠራበት የሚገባውን መክሊት ቀበረው፡፡ ይህም ለጌታው ትእዛዝ ያለውን ቸልተኝነት ያሳያል፡፡

ሁለተኛው ስሕተቱ ጌታው መክሊቱን በተቆጣጠረው ጊዜ የዐመፅ ቃል መናገሩ ነው፡፡ ጌታው ከሔደበት ቦታ ተመልሶ በተሰጠው መክሊት ምን እንዳደረገ ይህን አገልጋይ ሲጠይቀው፡- «አንተ ካልዘራህበት የምታጭድ፣ ካልበተንህበትም የምትሰበሰብ ጨካኝ ሰው እንደንህ አውቃለሁ፡፡ ስለ ፈራሁም ሔድሁና መክሊትህን በምድር ውስጥ ቀበርሁ፤» ሲል ነበር የመለሰለት፡፡ ይህ ምላሽ ከዐመፃ ባሻገር የሐሰት ቃልም አለበት፡፡ ምክንያቱም እርሱ እንዳለው ጌታው ካልዘራበት የሚያጭድ ካልበተነበት የሚሰበሰብ ጨካኝ ሰው ቢኾን ኖሮ ምንም መክሊት ሳይሰጠው ከነትርፉ ሁለት መክሊቶችን ይጠይቀው ነበር፡፡ ነገር ግን ተጽፎ የምናነበው ትርፉን ከመጠየቅ በፊት አንድ መክሊት ሰጥቶት እንደ ነበረ ነው፡፡ ይህ ማለት ደግሞ አስቀድሞ ገንዘቡን ዘርቶ ነበር ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ይህ ጌታ ዘርቷልና ማጨድ ይገባዋል፤ በትኗልና መሰብሰብም መብቱ ነው፡፡

ሦስተኛው ስሕተቱ ደግሞ ዕድሉን ለሌሎች አለመስጠቱ ሲኾን፣ ይህ አገልጋይ በተሰጠው መክሊት ነግዶ ማትረፍ ቢሳነው እንኳን ዕድሉን ለሌሎች መስጠት ሲገባው መክሊቱን ቆፍሮ ቀብሮታል፡፡ ይህ ሰው የተሰጠው መክሊት በትርፍ ሊመለስ እንደሚገባው ጠንቅቆ ያውቃል፡፡ ምክንያቱም ገና ሲቀበል ከጌታው የተቀበለው ትእዛዝ ነውና፡፡ ስለዚህ እርሱ መውጣት መውረዱ ቢከብደውም ወጥተው ወርደው ማትረፍ ለሚችሉ ሰዎች አለመስጠቱ ተጨማሪ ጥፋቱ ነው፡፡ ይህን እንዳያደርግ ያሰረው ደግሞ በውስጡ የተቀረፀው የዐመፅ መንፈስ ለመኾኑ ለጌታው የሰጠው ረብ የሌለው ምላሽ ማስረጃችን ነው፡፡

የአገልጋዮቹ ጌታ የእግዚአብሔር ምሳሌ እንደ ኾነ፤ ሦስቱ አገልጋዮች ደግሞ በተለያየ ደረጃ ያሉ ምእመናንን እንደሚወክሉ የቤተ ክርስቲያን መተርጕማን ያስተምራሉ፡፡ ከተጠቀሰው ታሪክ ከምንማራቸው ቁም ነገሮች መካከልም ሁለቱን እንመልከታለን፤

ለእያንዳንዳችን ከእግዚአብሔር የተሰጠን ጸጋ እንዳለ እንረዳበታለን

እግዚአብሔር አምላካችን እያንዳንዳችን በሃይማኖታችን ፍሬ እንድናፈራ ይፈልጋል፡፡ ፍሬ ማፍራት የምንችልበትን ኃይልና ጸጋ ደግሞ እርሱ ይሰጠናል፡፡ ከእግዚአብሔር ዘንድ የተቀበልናቸው ስጦታዎች በቍጥር እጅግ ብዙ ቢኾኑም በዓይነታቸው ግን በሁለት መክፈል እንችላለን፡፡ የመጀመሪያው እያንዳንዱ ክርስቲያን ዳግመኛ በመወለድ ምሥጢር ያገኘው የእግዚአብሔር ልጅነት ጸጋና ከልጅነት ጋር በተያያዘ የሚሰጠን ስጦታ ነው (ዮሐ.፫፥፫)፡፡ ሁለተኛው ደግሞ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድና እንደየአቅማችን ለመንፈሳዊ አገልግሎታችን ማስፈጸሚያ ይኾነን ዘንድ የሚሰጠን ስጦታ ነው፡፡ ለምሳሌ ትንቢት መናገር፣ በልዩ ልዩ ልሳናት መናገር፣ አጋንንትን ማስወጣት፣ ወዘተ. የመሳሰሉት ጸጋዎች (ስጦታዎች) ከዚህኛው ዓይነት ስጦታ የሚመደቡ ናቸው (፩ኛቆሮ.፲፪፥፬)፡፡

በመጀመሪያውም ይኹን በሁለተኛው ዓይነት ስጦታ በእኛ በተቀባዮች ዘንድ ብዙ የሚያሳዝኑ ችግሮች አሉ፡፡ ዳግመኛ በመወለድ ምሥጢር (በጥምቀት የሥላሴን ልጅ መኾን) ስላገኘው የልጅነት ጸጋ የሚያስብና በዚህም የሚደሰት ክርስቲያን ማግኘት አዳጋች ነው፡፡ ለዓመት በዓላት (ለመስቀል ደመራ፣ ለጥምቀት፣ ለፋሲካ፣ ወዘተ) ካልኾነ በስተቀር ክርስትናችን ትዝ የማይለን ክርስቲያኖች ጥቂቶች አይደለንም፡፡ እንደዚሁም ዘመዶቻችን ወይም ራሳችን ከዚህ ዓለም በሞት ስንለይ ካልኾነ በስተቀር በሕይወት ዘመናችን ወደ ቤተ ክርስቲያን ደጅ የማንደርስ ብዙዎች ነን፡፡ እግዚአብሔር ለእኛ የልጅነትን ጸጋ በመስጠቱ ለእኛ ያለውን ጥልቅ ፍቅሩን አሳይቶናል፡፡ ምክንያቱም ልጅነታችን ዋጋ ተከፍሎበታልና፡፡ እንዲሁ በቀላሉ አይደለም ልጆች የተባልነው፡፡

እኛ ልጅነትን እንድንቀበል አምላክ መከራን ተቀብሏል፡፡ የጥምቀታችን ውኃ የፈሰሰውም በጦር ከተወጋው ከጌታች ጎን ነው (ዮሐ.፲፱፥፳፬)፡፡ ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ ይኼንን ዅሉ ምሥጢር ሲያመለክት ‹‹የእግዚአብሔር ልጆች ተብለን ልንጠራ አብ እንዴት ያለውን ፍቅር እንደ ሰጠን እዩ፤›› በማለት ያደንቃል (፩ኛ ዮሐ.፫፥፩)፡፡ እኛ ልጆቹ እንኾን ዘንድ እግዚአብሔር ካሳየን የአባትነት ፍቅሩ ባሻገር ልጆቹ በመኾናችን መንግሥቱን እንድንወርስ መፍቀዱም ከአእምሮ በላይ ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለገላትያ ምእመናን በላከው መልእክቱ ‹‹እንኪያስ እናንተ ልጆች ናችሁ እንጂ ባሮች አይደላችሁም፡፡ ልጆች ከኾናችሁ በኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ወራሾች ናችሁ፤›› በማለት የሚነግረንም ይህንኑ ተስፋ ነው (ገላ.፬፥፯)፡፡

ትልቁ ችግር ተጠማቂው ሰው ይህን የልጅነት ክብር አለመረዳቱ ነው፡፡ የልጅነቴን ክብር ተረድቻለሁ እያለ የሚያወራውም ቢኾን የልጅነቱን መክሊት በልቡናው ውስጥ ቀብሮ አንድም ፍሬ ሳያፈራ ስለ ማንነቱ ለማውራት ቃላት ሲመርጥ ጊዜውን ያባክናል፡፡ አብዛኞቻችን ክርስቲያን የክርስትና እምነት ደጋፊዎች እንጂ ተከታዮች አይደለንም፡፡ የእግዚአብሔር ልጅነት ሊገለጥ የሚገባው ግን በምናሳየው የደጋፊነት (የቲፎዞነት) ስሜት አይደለም፡፡ ደጋፊነት የሚያስፈልገው በጊዜ እና በቦታ ለተወሰነ ያውም ኃላፊ ለኾነ ድርጊት ነው፡፡ ክርስትና ግን በማንኛውም ቦታና ጊዜ ልንኖርበት የሚገባ ዘለዓለማዊ የሕይወት መስመር ነው፡፡ ስለዚህ የመጀመሪያው መክሊታችን ልጅነታችን መኾኑን በሚገባ መረዳት ያስፈልገናል፡፡ በዚህ መክሊታችንም የታዘዝናቸውን ምግባራት ፈጽመን የሚጠበቅብንን ፍሬ ማፍራት አለብን፡፡ ካለዚያ መክሊቱን እንደ ቀበረው ሰው መኾናችን ነው፡፡

እያንዳንዱ ስጦታ እንደሚያስጠይቅ እንገነዘብበታለን

እግዚአብሔር ያለ አንድ ዓላማ በሓላፊነት ለሰዎች ስጦታን አልሰጠም፤ አይሰጥምም፡፡ ማንም ከእግዚአብሔር የተቀበለ ሰው የተሰጠው ስጦታ ለዓላማ ነውና ጥያቄ አለበት፡፡ ጠያቂው ደግሞ የስጦታው ባለቤት ራሱ እግዚአብሔር ነው፡፡ መንጋውን እንዲጠብቁለት ልዩ ልዩ የአገልግሎት ሰጦታዎችን እግዚአብሔር የሰጣቸው አሉ (ዮሐ. ፳፩፥፲፭፤ ገላ. ፩፥፲፭-፲፮)፡፡ ኾኖም ግን የተሰጣቸው ሓላፊነት የሚያስጨንቃቸው፤ ከልባቸው በትሕትና የሚተጉ ክርስቲያኖች የመኖራቸውን ያህል የሚያገለግሉበትን ስጦታ ከእግዚአብሔር መቀበላቸውን፣ ጸጋቸው የሚያስጠይቃቸው መኾኑን የዘነጉና መንገዳቸውን የሳቱም በርካታ ናቸው፡፡

በእግዚአብሔርና በሰዎች መካከል እንደ ድልድይ ኾነው ያገለግሉበት ዘንድ በተሰጣቸው ሥልጣን እግዚአብሔርን የሚያሳዝን ተግባር የሚፈጽሙ አገልጋዮች ለዚህ ጥሩ ምሳሌዎች ናቸው፡፡ ሕዝበ ክርስቲያኑን ወደ እግዚአብሔር ከመምራት ይልቅ የነሱ ደጋፊ፣ ስለ ክብራቸው ተሟጋች እንዲኾን፤ እርስበርስ ጎራ እንዲፈጥርና ‹‹የጳውሎስ ነኝ፤ የአጵሎስ ነኝ›› በሚል ከንቱና የማይጠቅም ሐሳብ እንዲከፋፈል የሚያደርጉ ሰባኪዎችም አይታጡም፡፡ በአጠቃላይ ዅላችንም በተሰጠን መክሊት ባለቤቱ ከፊቱ አቁሞ ስለሚጠይቀን ከገብር ኄር ታሪክ በጎ አገልጋይነትን ተምረን፣ በክርስቲያናዊ ምግባር ጸንተን፣ እንደየአቅማችን መልካም ፍሬን ማፍራት ይጠበቅብናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

እንደ ገብር ኄር ታማኝ አገልጋዮች እንኹን

በአያሌው ዘኢየሱስ 

መጋቢት ፲፰ ቀን ፳፻፱ .

ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመዋዕለ ሥጋዌው ለሕዝቡና ለደቀ መዛሙርቱ ትምህርቱን ቃል በቃል ወይም በሰምና ወርቅ ወይም በምሳሌ አስተምሮአቸዋል፡፡ ሲያስተምርም በተለያዩ የሙያ ዘርፎች ላይ የተለያዩ ምሳሌዎችን በማቅረብና ምሥጢሩን በማስረዳት ነበር፡፡ ስለዚህም ቃሉን ለገበሬዎች በዘርና በእንክርዳድ፤ እንደዚሁም በሰናፍጭ ቅንጣት፤ ለእናቶች በእርሾ፤ ለነጋዴዎች በመዝገብና በዕንቍ፤ ለዓሣ አጥማጆች በመረብ፤ ወዘተ. እየሰመሰለ ያስተምራቸው ነበር፡፡ በተመሳሳይ መልኩ በዐሥሩ ቆነጃጅት፤ በሰርግ ቤት፤ በበግና በፍየል፤ ወዘተ. እየመሰለ ስለ መንግሥቱ በስፋት አስተምሯል፡፡ ጌታ ትምህርቱን በምሳሌ ያስተምር የነበረው አስቀድሞ፡- «አፌን በምሳሌ እከፍታለሁ፤ ከቀድሞ ጀምሮ ያለውንም ተምሳሌት እናገራለሁ፤» ተብሎ በነቢዩ ዳዊት እንደ ተነገረ (መዝ.፸፯፥፪)፣ ቃሉን የሚሰሙት ዅሉ ትምህርቱ ሳይገባቸው እየተጠራጠሩ ወደ ቤታቸው እንዳይመለሱና ምሥጢሩ ግልጽ እንዲኾንላቸው ለማድረግ ነበር፡፡

በዐቢይ ጾም ስድስተኛ ሳምንት በቤተ ክርስቲያን የሚቀርበው ንባብ፣ ስብከትና መዝሙር የሚያስረዳን ምሥጢርም ስለ አንድ በጎ እና ታማኝ አገልጋይ በምሳሌ የተነገረውን ትምህርት ነው፡፡ በዚህ የወንጌል ንባብ ውስጥ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመጨረሻው የፍርድ ቀን ሰዎች እንደ ሥራቸው መጠን እንደሚዳኙ በምሳሌ አስተምሯል፡፡ በዚህ ምሳሌ አንድ ጌታ ለሦስት አገልጋዮቹ ለአንዱ አምስት፤ ለአንዱ ሁለት እና ለሌላው ደግሞ አንድ መክሊት ከሰጣቸው በኋላ ነግዱና አትርፉ በማለት እርሱ ወደ ሌላ አገር መሔዱ ተገልጦአል፡፡ አምስት መክሊት የተቀበለው የመጀመሪያው አገልጋይ በተሰጠው አምስት መክሊት ቆላ ወርዶ፣ ደጋ ወጥቶ ከነገደ በኋላ አምስት ተጨማሪ መክሊቶችን በማትረፍ ዐሥር መክሊት አኖረ፡፡ ሁለተኛውም በተሰጡት አምስት መክሊቶች ከነገደ በኋላ ሌሎች ተጨማሪ ሁለት መክሊቶችን አትርፎ አስቀመጠ፡፡ ሦስተኛው ግን እንደ ሁለቱ አገልጋዮች ሳይወጣና ሳይወርድ፣ ሳይደክምና ሳያተርፍ በአቅሙ መጠን በተሰጠው አንድ መክሊት ሥራ ሳይሠራ መክሊቱን በጉድጓድ ቀበረው፡፡

ይህ ዅሉ ከኾነ በኋላ ለእነዚህ ሦስት ባሪያዎች በመጠን የተለያዩ መክሊቶችን ሰጥቶ ወደ ሩቅ አገር ሔዶ የነበረው ጌታቸው ወደ እነርሱ ተመልሶ መጣ፡፡ ከዚያም እያንዳንዳቸውን በየተራ እየጠራ በተሰጧቸው መክሊቶች ምን እንደ ሠሩ ጠየቃቸው፤ ተቆጣጠራቸው፡፡ በዚህ መሠረት አምስት መክሊቶችን የተቀበለው የመጀመሪያው አገልጋይ በጌታው ፊት ቀርቦ በተሰጡት አምስት መክሊቶች አምስት በማትረፍ ዐሥር መክሊቶችን ለጌታው አስረከበ፡፡ ሁለተኛውም እንዲሁ ሌሎች ሁለት መክሊቶችን አትርፎ አራት መክሊቶች ለጌታው አስረከበ፡፡ በዚህ ጊዜ የእነዚህ ሁለት አገልጋዮች ጌታ በእነርሱ ደስ በመሰኘቱ፡- ‹‹አንተ መልካም፣ በጎ እና ታማኝ ባርያ! በጥቂቱ ታምሃልና በብዙ ስለምሾምህ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ!›› በማለት ሁለቱንም ወደ መንግሥቱ አስገባቸው፡፡

የተሰጠውን አንድ መክሊት ምንም ሥራ ሳይሠራና ሳያተርፍበት ጉድጓድ ውስጥ የቀበረው ሦስተኛው አገልጋይ ግን፡- ‹‹ጌታ ሆይ፣ ካልዘራህበት የምታጭድ፤ ካልበተንህበት የምትሰበስብ ጨካኝ ሰው መኾንህን ስለማውቅና ስለ ፈራሁ መክሊትህን ጉድጓድ ቆፍሬ በመቅበር አቆይቼልሃለሁና እነሆ ተረከበኝ!›› አለው፡፡ በዚህ ጊዜ ንጉሡ እጅግ ተቆጥቶ፡- ‹‹አንተ ክፉና ሐኬተኛ ባርያ! በእርግጥ እንዲህ ዓይነት ሰው መኾኔን ካወቅህ ገንዘቤን ለሚነግዱበት ወይም ለሚለውጡ ሰዎች በመስጠት እንዲያተርፉበት ማድረግና ተመልሼ ስመጣ ከነትርፉ ከእነርሱ መቀበል እችል ነበር፡፡ አንተ ይህን ሳታደርግ ጭራሹኑ በድፍረት እነዚህን በእውነት ላይ ያልተመሠረቱ ክፉ ቃላትን ስለ ተናገርህ ቅጣት ይገባሃል!›› ሲል መለሰለት፡፡ ከዚያም፡– ‹‹ያለውን መክሊት ውሰዱና ዐሥር መክሊት ላተረፈው ጨምሩለት፤ላለው ይሰጠዋል፤ ይበዛለትማል፡፡ ከሌለው ግን ያው ያለው እንኳ ይወሰድበታል፡፡ ስለዚህ የማይጠቅመውን ባሪያ ወደ ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ወዳለበት ወደ ውጪ አውጡት!›› ብሎ ለወታደሮቹ አሳልፎ ሰጠው፡፡

በዚህ የወንጌል ቃል «ወደ ሌላ አገር የሚሔድ ሰው» ተብሎ የተጠቀሰው ባለጠጋ ቅን ፈራጅ የኾነው የጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ ነው፡፡ በምሳሌው ውስጥ የተጠቀሱት አገልጋዮች የሚወክሉት ምእመናንን ወይም እኛን ነው፡፡ መክሊት የተባለው ደግሞ በጎ የሚያሰኘው መልካም ሥራ ነው፡፡ የመጀመሪያዎቹ ሁለት ባሪያዎች ወይም አገልጋዮች ምግባርን ከሃይማኖት ጋር አስተባብረው በያዙ ጻድቃን ይመሰላሉ፤ መክሊቱን ጉድጓድ በመቆፈር የቀበረው ክፉና ሐኬተኛ አገልጋይ ደግሞ ምግባርና ሃይማኖት የሌላቸው ኃጥአን ምሳሌ ነው፡፡

ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአጭር ቁመት፣ በጠባብ ደረት ተወስኖ፣ በመካከላችን ተገኝቶ ወንጌለ መንግሥቱን ከሰበከልን በኋላ ለእያንዳንዳችን አንድ፣ ሁለትና አምስት መክሊቶችን በመስጠት ‹‹ለፍርድ እስከምመጣ ደረስ ነግዳችሁና አትርፋችሁ ጠብቁኝ›› ብሎን በዕርገቱ ወደ ቀደመ ክብሩ ተመልሶ  ሔዷል፡፡ ዅላችንም ከእግዚአብሔር የተለያዩ መክሊቶችን ተቀብለናል፤ እንድንነግድባቸውና እንድናተርፍባቸው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ይህን አስመልክቶ ቃሉን ባስተማረበት መልእክቱ እንዲህ ብሏል፤ ‹‹ለአንዱ ጥበብን መናገር በመንፈስ ይሰጠዋልና፤ ለአንዱም በዚያው መንፈስ ዕውቀትን መናገር ይሰጠዋል፡፡ ለአንዱም በዚያው መንፈስ እምነት፤ ለአንዱም በአንዱ መንፈስ የመፈወስ ስጦታ፤ ለአንዱም ትንቢትን መናገር፤ ለአንዱም መናፍስትን መለየት፤ ለአንዱም በልዩ ዓይነት ልሳን መናገር፤ ለአንዱም በልሳኖች የተነገረውን መተርጐም ይሰጠዋል፡፡ ይህን ዅሉ ግን ያ፣ አንዱ መንፈስ እንደሚፈቅድ ለእያንዳንዱ ለብቻው እያካፈለ ያደርጋል፤» (፩ኛ ቆሮ.፲፪፥፰-፲፩)፡፡

እግዚአብሔር ለልጆቹ የሰጣቸው መክሊት ብዙ ነው፤ ለአንዱ የመስበክ፣ ለሌላው የማስተማር፣ ለሌላው የመቀደስ፣ ለሌላው የመዘመርመ ለሌላው የመባረክ፣ ለሌላው የማገልገል፣ ወዘተ. መክሊቶችን ወይም ልዩ ልዩ ጸጋን ሰጥቶአል፡፡ አንድ ሰው የሚሰጠው አንድ መክሊት ብቻ አይደለም፡፡ ሁለት ወይም ሦስት ወይም ከዚያ በላይ መክሊቶች ሊሰጡት ይችላል፡፡ በፍርድ ቀን ዅሉም ሰው የሚፈረድበትም በተሰጠው መክሊት ትርፍ መሠረት ነው፡፡ በተቀበለው መክሊት የሚያተርፍ ሰው በፍርድ ቀን በኢየሱስ ክርስቶስ፡- ‹‹መልካም፤ አንተ በጎ፣ ታማኝም ባርያ! በጥቂቱ ታምነሃል፤ በብዙም እሾምሃለሁ፡፡ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ!›› የሚል ቃል ይሰማል፡፡ መክሊቱን መሬት ቆፍሮ የሚቀብር አገልጋይ ግን በውጪ ባለው ጨለማ ውስጥ ተጥሎ በዚያ በልቅሶና ጥርስ በማፋጨት እንዲቆይ ይደረጋል፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ እንደ ተናገረው ዅሉም ከእግዚአብሔር ዘንድ የተለያዩ ስጦታዎችን ወይም መክሊቶችን ተቀብሏል፡፡ ይኹን እንጂ ዅሉም መክሊቱን ቆፍሮ ስለ ቀበረ ለእግዚአብሔር ምንም ሊያተርፍ አልቻለም፡፡ በወንጌል ላይ የተጠቀሰው ክፉና ሐኬተኛ አገልጋይ የተሰጠውን መክሊት ምንም ዓይነት ሥራ ሳይሠራበት ወይም ሳይነግድበት ወይም ሳያተርፍበት በመሬት ውስጥ ቆፍሮ በማስቀመጡና ጌታው ሲመጣ ያለ ትርፍ በማስረከቡ በዚህ ዘመን ከምንገኝ ሰዎች እጅጉን ይሻላል፡፡ ምክንያቱም እኛ መክሊቶቻችንን ጠብቀን በማቆየት ለእግዚአብሔር ማስረከብ እንኳ አልቻልንምና፡፡ ዛሬ መክሊት የተቀበለ ዅሉ መክሊቱን ቀብሯል ወይም ጥሏል ለማለት ያስደፍራል፡፡ አንድ የእግዚአብሔር አገልጋይ በተሰጠው የመቀደስ መክሊት መቀደስ ሲገባው የሚዘፍን ከኾነ መክሊቱን ጥሏል፡፡

አንድ የመዘመር መክሊት የተሰጠው አገልጋይ ለእግዚአብሔር መዘመር ሲገባው የሚዘፍን ወይም ሰዎችን የሚያማ ወይም የሚሳደብ ከኾነ መክሊቱን ጥሏል፡፡ ትክክለኛውን የወንጌል ትምህርት እንዲያስተምርና ሰዎችን በንስሐ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት እንዲያስገባ የማስተማር መክሊት ከኢየሱስ ክርስቶስ የተቀበለ ሰባኬ ወንጌል የኑፋቄ ትምህርት በማስተማር የዋሃንን ወደ ሲኦል የሚመራ ከኾነ መክሊቱን ጥሎታል ወይም አጥፍቶታል እንጂ አልቀበረውም፡፡ በተሰጠው የመባረክ መክሊት ወይም ሥልጣን ምእመናንን መባረክና ኃጢአታቸውን መናዘዝ ሲገባው ለጥንቆላ ሥራ ተቀምጦ እፈርዳለሁ የሚል ከኾነ መክሊት የተባለ ክህነቱን አቃሎአታል፤ አጥፍቷታል እንጂ አልቀበራትም፡፡ በእግዚአብሔር ዐውደ ምሕረት ላይ ወንጌልን መናገር ሲገባው ተራ ወሬ ወይም ፖለቲካ የሚደሰኩር ከኾነ ይህ ሰው መክሊቱን ጥሏል፡፡ ሌሎቹም እንደዚሁ፡፡ ለዚህ ነው በዚህ ዘመን ያለን ሰዎች መክሊቱን ከቀበረው ሰው ያነስን፤ ክፉዎች እና ሐኬተኞች ነን የምንለው፡፡

እግዚአብሔር አምላካችን በወንጌል እንደ ተነገረለት ለጻድቃን ሊፈርድላቸውና በኃጥአን ሊፈርድባቸው ዳግመኛ ወደ ምድር ይመጣል፡፡ ከፍርዱ በፊት ዅላችንንም በሰጠን መክሊቶች መጠን ይቆጣጠረናል፡፡ ስለዚህም አንድ መክሊት የተሰጠን ሁለትና ከዚያ በላይ፤ ሁለት የተሰጠን ሁለት ወይም ከዚያ በላይ፤ አምስት የተቀበልነውም አምስትና ከዚያም የሚበልጡ መክሊቶችን ማትረፍ ይጠበቅብናል፡፡ ለመኾኑ በተሰጠን መክሊት እኛ ያተረፍነው ምንድር ነው? በዕርቅ ፋንታ ጠብን የምናባብስ ከኾንን በመክሊታችን ሰዎችን አጉድለናል እንጂ ማትረፍ አልቻልንም፡፡ በመመረቅ ፋንታ የምንራገም ከኾንን መክሊታችንን ጥለናል፡፡ በመጸለይ ፋንታ ለመደባደብ የምንጋበዝ ከኾነም የተሰጠንን መክሊት አጥፍተናል፡፡ የገብር ኄርን ሰንበት ዛሬ ስናከብር አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተገልጦ እያንዳንዳችንን፡- ‹‹ታተርፉበት ዘንድ የሰጠኋችሁን መክሊት እስከነትርፉ አስረክቡኝ!› ቢለን ምንድር ነው የምናስረክበው? ለጥያቄው የምንሰጠውስ ምላሽ ምን የሚል ይኾን?

በወንጌል የተጠቀሰው ያ፣ ሰነፍ አገልጋይ መክሊቱን መቅበሩ ሳያንሰው ለጌታው የሰጠው ክፉ መልስ ለከፍተኛ ቅጣት ዳርጎታል፡፡ ለጌታው፡- «ካልዘራህበት የምታጭድ፤ ካልበተንህበትም የምትሰበስብ ጨካኝ ሰው መኾንህን አውቃለሁ፤» የሚል ምላሽ ነበር የሰጠው፡፡ በዘመናችን ያሉ አንዳንድ ሰዎችም ከዚህ ሰው ጋር የሚመሳሰል ጠባይ አላቸው፤ እነርሱ ስለ እግዚአብሔር ባሕርይ ምንም ነገር ሳያውቁ የእግዚአብሔርን ጠባይና ዕውቀት በእነርሱ የዕውቀት ሚዛን ለመመዘን ይሞክራሉና፡፡ አንድ ክርስቲያን በጠና ሕመም ሲታመም ወይም ከልጆቹ አንዱ በሞት ሲለይበት ወይም ንብረቱ በእሳት ቃጠሎ ሲወድም ይህን አደጋ ያደረሰበት እግዚአብሔር እንደ ኾነ አድርጎ በማሰብ የማይገቡ ቃላትን በእግዚአብሔር ላይ የሚሰነዝሩ ሰዎች አሉ፡፡ እንደ እነዚህ ዓይነት ሰዎች በእግዚአብሔር ህልውና ላይ በመምጣት «እግዚአብሔር ቢኖር ኖሮ ይህ ሕመም ወይም አደጋ በእኔ ላይ አይደርስም ነበር፤» ይላሉ፡፡ ከዚህ በተጨማሪ «እግዚአብሔር እንደዚህ የጨከነብኝ ምን አድርጌው ነው እያሉ እግዚአብሔርን እንደ ሐኬተኛው አገልጋይ ጨካኝ አምላክ የሚያደርጉት ሰዎችም አሉ፡፡

የጻድቁ የኢዮብ ሚስት በእግዚአብሔር ላይ በልቧ ስትሰነዝራቸው የነበሩ ቃላትን ይደግማቸው ዘንድ «እግዚአብሔርን ስደበውና ሙት» በማለት በእርሱ ላይ ልታነሣሣው ሞክራ ነበር፡፡ ነገር ግን «የለም» ወይም «ጨካኝ ነው» ብሎ በድፍረት እግዚአብሔርን መናገር ጥርስ ማፋጨት ወዳለበት ጨለማ የሚያስገባ ክፉ ቃል መኾኑን እናስተውል፡፡ በመሠረቱ ሊነቀፍ ወይም ሊወገዝ ወይም ሊኮነን የሚገባው ሰይጣን እንጂ እግዚአብሔር አይደለም፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ቸር፣ ርኅሩኅ፣ ታጋሽ፣ ይቅር ባይ፣ መዓቱ የራቀ፤ ምሕረቱ የበዛ አምላክ ነው፡፡ እርሱ በዚህ ምድር ላይ ስንኖር ያልዘራነውን የጽድቅ ፍሬ እንድንዘራና እንድናጭድ፤ ያልበተንነውንም መልካም ዘር በመበተን በፍርድ ቀን ምርቱን እንድንሰበስብ የሚፈልግ ጌታ ነው፡፡ እኛ ሠላሳ፣ ስድሳና መቶ ፍሬ በማፍራት የእነዚህ ፍሬዎችን ምርት በመሰብሰብ ሰማያዊ መንግሥቱን እንድንወርስ ይፈልጋል፡፡ እርሱ ለሚያምኑትና ለሚታመኑት ዅሉ ታማኝ ነው፤ የሚያምኑትን የሚክድ ጨካኝ ፈጣሪ አይደለም፡፡ ካልዘራበት የሚያጭድና ካልበተነበት የሚሰበስብ ሰው እንጂ እግዚአብሔር አይደለም፤ ጨካኝ፣ ከሀዲና የማይታመንም ሰው ነው፡፡

ዛሬ እግዚአብሔር በጎ እና ታማኝ አገልጋይ አጥቶአል፡፡ ዛሬ ቤተ ክርስቲያን የሚታመን አገልጋይ አጥታለች፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ፡- «ዅሉ ዐመፁ፤ በአንድነትም ረከሱ፡፡ በጎ ነገርን የሚሠራ የለም፤ አንድም ስንኳ፤» (መዝ ፲፫፥፫) ተብሎ የተነገረው ለዚህ ዘመን አገልጋዮች ነው፡፡ የሰው ልጅ ለእግዚአብሔርና ለቤተ ክርስቲያን ታማኝ አገልጋይ ሊኾን አልቻለም፡፡ ቤተ ክርስቲያን በቃሉ የሚገኝ ሰው ለማግኘት ተቸግራለች፡፡ በጥቂቱ ታምኖ በብዙ ላይ ሊሾም የሚችል ሰው ስለ ጠፋ ቤተ ክርስቲያን ‹‹የሰው ያለህ!›› እያለች ነው፡፡ ለምእመናን መዳንና ወደ እግዚአብሔር መንግሥት መግባት የሚተጉ አገልጋዮች ቍጥር እየቀነሰ ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላክ አገልጋዮችን በቤተ ክርስቲያን ላይ የሾማቸውና የሚሾማቸው ግን ራሳቸውን፣ ቤተ ክርስቲያንንና መንጋውን ከጥፋት እንዲጠብቁ ነበር (ሐዋ. ፳፥፳፰)፡፡ ሕዝቡን ለመጠበቅ ተሹሞ የሚያጠፋ ጠባቂ ዕድል ፈንታውና ዕጣ ተርታው ትሉ በማያንቀላፋበትና እሳቱ በማይጠፋበት ዘላለማዊ ሲኦል ውስጥ ነው፡፡ ይህን የሚያደርግ አገልጋይ ቅጣቱ ዘላለማዊ መኾኑን ከወዲሁ ሊያውቅ ይገባዋል፡፡

አምላካችን በዳግም ምጽአቱ እስከሚገለጥ ድረስ መንጋውን በመመገብ፣ ውኃ በማጠጣትና በማሳረፍ ፋንታ ለራሱ ብቻ የሚበላና የሚጠግብ፤ የሚጠጣና የሚሰክር፤ የሚያርፍና የሚዝናና ከኾነ እግዚአብሔር ዕድሉን ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ባለበት ጨለማ ውስጥ ያደርግበታል (ማቴ. ፳፬፥፵፭-፶፩)፡፡ ቤተ ክርስቲያንን በተለያያ መልኩ የሚዘርፍና እግዚአብሔርን የሚያሳዝን አገልጋይም ኾነ ተገልጋይ ከዚህ ጠባዩ ሊቆጠብ ይገባዋል፡፡  የቤተ ክርስቲያን አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ መከራ የተቀበለው ለዚህች ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ነው፡፡ በጥፊ የተመታው፤ ርኩስ ምራቅ የተተፋበት፤ የእሾኽ አክሊል የተቀዳጀው፤ በአጠቃላይ የተንገላታውና የሞተው ለዚህች ቤተ ክርስቲያንና ለምእመናን ነው፡፡ ስለ ኾነም ካህናትም ምእመናንም በጎ እና ታማኝ አገልጋዮች ልንኾን ይገባናል፡፡

የአምላካችን የእግዚአብሔር አብ ፍቅር፣ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ እና የመንፈስ ቅዱስ ኅብረት ከእኛ ጋር ይኹን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ገብር ኄር (ለሕፃናት)

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

መጋቢት ፲፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

እንደምን ሰነበታችሁ የተወደዳችሁ ሕፃናት? መልካም! እስከ ዛሬ ድረስ የጠበቀን፣ ለወደፊትም የሚጠብቀን አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር ይመስገን! ልጆች! ስድስተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ‹ገብር ኄር› የሚል ስያሜ አለው፡፡ ‹ገብር ኄር› ማለት ‹በጎ፣ ታማኝ አገልጋይ› ማለት ነው፡፡

በዚህ ሳምንት ጸጋን (ተሰጥዎን) በአግባቡ ስለ መጠቀም እና ስለ መንፈሳዊ አገልግሎት የሚያስተምር ቃለ እግዚአብሔር በቤተ ክርስቲያን ይነገራል፡፡ በተጨማሪም ስለ ‹ገብር ሐካይ› ጠባይ የሚያስረዳ ትምህርት ይቀርባል፡፡ ‹ገብር ሐካይ› ማለት ‹ሰነፍ አገልጋይ› ማለት ነው፡፡ የእነዚህን ሰዎች ታሪክም በአጭሩ እናስታውሳችኋለን፤ በማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ ፳፭ ከቍጥር ፲፬ ጀምሮ እንደ ተጻፈው አንድ ሰው አገልጋዮቹን ጠራና ለአንዱ አምስት፤ ለአንዱ ሁለት፤ ለአንዱ ደግሞ አንድ መክሊት ሰጣቸው፡፡ ልጆች! ‹መክሊት› – ብር፣ ዶላር፣ እንደሚባለው ያለ የገንዘብ ዓይነት ነው፡፡

አምስት መክሊት የተቀበለው አገልጋይ ነግዶ፣ ሌላ አምስት መክሊት አትርፎ ዐሥር አድርጎ ለጌታው አቀረበ፡፡ ጌታውም፡- ‹‹አንተ ጎበዝ እና ታማኝ አገልጋይ! በጥቂቱ ታምነሃልና በብዙ እሾምሃለሁ፤ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ!›› አለው፡፡ ሁለት መክሊት የተቀበለውም አትርፎ አራት አድርጎ አቀረበ፡፡ እርሱንም ጌታው፡- ‹‹አንተ ታማኝ አገልጋይ በጥቂቱ ታምነሃልና ወደ ጌታህ ደስታ ግባ!›› አለው፡፡ እርሱ ግን መክሊቱን ቀብሮ አቆየና ጌታው እንዲያስረክብ በጠየቀው ጊዜ፡- ‹‹እነሆ መክሊትህ!›› ብሎ ምንም ሳያተርፍበት መለሰለት፡፡ ጌታውም፡- ‹‹ይህን ክፉና ሰነፍ አገልጋይ እጅ እግሩን አስራችሁ ጨለማና ጥርስ ማፋጨት ወዳለበት ሥፍራ ውሰዱት! መክሊቱን ቀሙና ለባለ ዐሥሩ ጨምሩለት!›› ብሎ አዘዘ፡፡ ‹ገብር ሐካይ› የተባለው ይህ መክሊቱን የቀበረው አገልጋይ ነው፡፡

ልጆች! ከእግዚአብሔር ዘንድ የተሰጠንን ጸጋ በአግባቡ ከተጠቀምን ትልቅ ዋጋ እንደምናገኝ፤ ጸጋችንን በአግባቡ ካልተጠቀምን ደግሞ ቅጣት እንደምንቀበል ከዚህ ታሪክ እንማራለን፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን ለእናንተም ስታድጉ በመንፈሳዊው ሕይወታችሁ የጵጵስና፣ የቅስና፣ የዲቁና፣ የሰባኪነት፣ የዘማሪነት፣ ወዘተ. የመሳሰሉ ጸጋዎችን እንደየአቅማችሁ ይሰጣችኋል፡፡ በዓለማዊው ሕይወታችሁ ደግሞ የፓይለትነት፣ የመሐንዲስነት፣ የዶክተርነት፣ የመምህርነት፣ የመንግሥት ሠራተኛነት፣ ወዘተ. ሌላም ዓይነት የሥራ ጸጋ ያድላችኋል፡፡

መንፈሳዊውን ወይም ዓለማዊውን ትምህርታችሁን በርትታችሁ በመማር ካጠናቀቃችሁ በኋላ ከእናንተ ብዙ ሥራ ይጠበቃል፡፡ ስለዚህ ልጆች! በምድር ሕይወታችሁ እንዲባረክ፤ በሰማይም የእግዚአብሔርን መንግሥት እንድትወርሱ እንደ ገብር ኄር የተሰጣችሁን ጸጋ በመጠቀም ቤተሰባችሁን፣ አገራችሁንና ቤተ ክርስቲያናችሁን በቅንነት ማገልገል አለባችሁ፡፡ በጣም ጥሩ ልጆች! ለዛሬው በዚህ ይበቃናል፤ በሌላ ዝግጅት እስከምንገናኝ ድረስ ሰላመ እግዚአብሔር ከእናንተ ጋር ይኹን! ሳምንቱ መልካም የትምህርት ጊዜ ይኹንላችሁ!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የዐቢይ ጾም ሳምንታት (ለሕፃናት) – ክፍል አራት

፮. ገብር ኄር

በልደት አስፋው

መጋቢት ፲፮ ቀን ፳፻፱ .

ሰላም ናችሁ ልጆች? ባለፈው ዝግጅት ስለ ደብረ ዘይት ተምረናል፡፡ ዛሬ ደግሞ ስለ ‹ገብር ኄር› እንማራለን፡፡ ስድስተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት (እሑድ) ‹ገብር ኄር› ይባላል፡፡ ትርጕሙ ‹ታማኝ፣ በጎ፣ ደግ አገልጋይ› ማለት ነው፡፡ ልጆች! አንድ ባለጠጋ አገልጋዮቹ ነግደው እንዲያተርፉበት ለአንዱ አምስት፤ ለሁለተኛው ሁለት፤ ለሦስተኛው አንድ መክሊት ሰጣቸው፡፡ ልጆች! ‹መክሊት› የገንዘብ ስም ነው፡፡

ከዚያ በኋላ አምስት እና ሁለት መክሊት የተቀበሉት ሁለቱ አገልጋዮች በተሰጣቸው መክሊት ነግደው እጥፍ አትርፈው ለባለ ጌታው አስረከቡ፡፡ ስለዚህም ገብር ኄር (ታማኝ አገልጋይ) ተብለው ተመሰገኑ፤ ልዩ ክብርን አገኙ፡፡ አንድ መክሊት የተቀበለው አገልጋይ ግን የተቀበለውን መክሊት ቀብሮ ካቆየ በኋላ ምንም ሳያተርፍበት ለጌታው አስረከበ፡፡ ይህ አገልጋይ ‹ገብር ሐካይ› ይባላል፡፡ ‹ሰነፍ አገልጋይ› ማለት ነው፡፡ በመክሊቱ ባለማትረፉ የተነሣ ቅጣት ተፈርዶበታል፡፡

የማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ ፳፭ ቍጥር ፲፬-፵፮ ያለውን የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ብታነቡት ሙሉ ታሪኩን ታገኙታላችሁ፡፡ ልጆች! ስድስተኛው የዐቢይ ጾም እሑድ ስለ እነዚህ አገልጋዮች እና ስለ መንፈሳዊ አገልግሎት ጥቅም ትምህርት የሚቀርብት ሳምንት በመኾኑ ‹ገብር ኄር› ተብሏል፡፡ እናንተም በተሰጣችሁ ጸጋ ብዙ ምግባር መሥራት አለባችሁ እሺ? መልካም ልጆች! ለዛሬው በዚህ ይበቃናል፡፡ በቀጣይ ደግሞ ስለ ኒቆዲሞስ እንማማራለን፡፡ ሰላመ እግዚአብሔር ከዅላችን ጋር ይኹን!

‹‹መኑ ውእቱ ገብር ኄር፤ ታማኝ አገልጋይ ማነው?››

በመ/ ምስጢረ ሥላሴ ማናየ

መጋቢት ፲፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስያሜ የዐቢይ ጾም ስድስተኛው እሑድ ወይም ሳምንት ‹ገብር ኄር› ይባላል፡፡ ሰያሜውን የሰጠውም ኢትዮጵያዊ ሊቅ ቅዱስ ያሬድ ነው፡፡ ከአምስቱ መጻሕፍቶቹ አንዱ በኾነው ጾመ ድጓ መጽሐፍ ሳምንቱን የዐቢይ ጾም ሳምንታት ስያሜዎች ከነሥርዓተ ማኅሌቱ አዘጋጅቷል፡፡ ስለዚህ በስድስተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ከዋዜማው ቅዳሜ ጀምሮ በቤተ ክርስቲያን የሚዘመረው ዝማሬ፣ የሚሰበከው ስብከት፣ የሚሰጠው ትምህርት ገብር ኄርን የሚያወሳ ነው ማለት ስለ ታማኝ አገልጋይ የሚያስረዳ ነው፡፡ በማቴዎስ ወንጌል ፳፭፥፲፬-፳፭ የተገለጸውና በዕለቱ የሚነበበው ወንጌል የሚነግረንም ይህንኑ ትምህርት ነው፡፡

አንድ ባዕለ ጸጋ ሰው ባሪያዎችን ጠርቶ ለአንዱ አምስት መክሊት ሰጠው፣ ሁለት መክሊት የሰጠውም አለ፣ አንድ መክሊትም የሰጠው አለ፡፡ ከዚህ በኋላ ወደሩቅ አገር ሔደ፡፡ አምስት መክሊት የተቀበለውም ወጥቶ ወርዶ ሌላ አምስት አትርፎ ዐሥር አደረገ፡፡ ሁለት የተቀበለውም አትርፎ አራት አደረገ፡፡ አንድ የተቀበለው ግን መሬቱን ቆፍሮ በሻሽ ጠቅልሎ የጌታውን መክሊት ቀበራት፡፡ ከብዙ ጊዜ በኋላ ጌታቸው መጥቶ ተቆጣጠራቸው፡፡ አምስት መክሊት የተቀበለው ቀርቦ ‹‹ጌታዬ አምስት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር እነሆ አምስት አተረፍኩ›› አለው፡፡ ‹‹ገብር ኄር ወምዕመን ዘበውሁድ ምእምነ ኮንከ ዲበ ብዙህ እሰይመከ ባእ ውስተ ፍሥሐሁ ለእግዚእከ፤ አንተ ታማኝ ባሪያ! በጥቂቱ ታምነሃልበብዙ እሾምሃለሁ፡፡ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ!›› አለው፡፡ ሁለት የተቀበለውም ቀርቦ ‹‹ጌታዬ ሁለት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር እነሆ ወጥቼ ወርጄ ሌላ ሁለት አትርፌ አራት አድርጌአለሁ፤›› ብሎ መክሊቱን አቀረበ፡፡ ጌታውም፡- ‹‹አንተ ታማኝ በጎ አገልጋይ በጥቂቱ ታምነሃልበብዙ እሾምሃለሁ፡፡ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ!›› አለው፡፡

አንድ መክሊት የተቀበለው ግን ‹‹ጌታዬ፣ አንተ ክፉና ጨካኝ፤ ካልዘራህበት የምታጭድ፤ ካልበተንህበት የምትሰበስብ፤ እንደ ኾንክ ስለ አወቅሁ መሬቱን ቆፍሬ ቀበርኋት እነኋት መክሊትህ›› አለው፡፡ ‹‹አንተ ሰነፍ ባሪያ! መክሊቴን በጊዜ ልትሰጠኝ በተገባህ ነበር፡፡ እኔም ወጥቶ ወርዶ ለሚያተርፍ በሰጠሁት ነበር፤›› አለና ‹‹ኑ፤ የዚህን ሐኬተኛ መክሊት ውሰዱና ዐሥር መክሊት ላለው ስጡት፡፡ላለው ይሰጡታል ይጨመርለታል ለሌለው ግን ያለውን ይቀሙታል›፡፡ ንዑ ይህን ሰነፍና ሐኬተኛ ባርያ እጅ እግሩን አሥራችሁ ጽኑ ጨለማ ወደ አለበት ውሰዱት! ጩኸትና ጥርስ ማፋጨት ወዳለበት ጨምሩት!›› የሚል ፍርድ ወሰነበት፡፡

ባዕለ ጸጋ የተባለው ጌታ ነው፡፡ መክሊት የተባለው ልዩ ልዩ የአገልግሎት ጸጋ ነው፡፡ ያተረፉት በሚገባ በታማኝነት ያገለገሉ ቅዱሳን ሰዎች ናቸው መክሊቱን የቀበረው ደግሞ በታማኝነት በተሰጠው ጸጋ ማገልገል ሲገባው ያላገለገለ ነው፡፡ ጌታቸው ሊቆጣጠራቸው መጣ ማለት ጌታችን በዕለተ ምጽአት ለዅሉም በሠራው ምግባር መጠን ዋጋ ለመስጠት እንደሚመጣ ያሳየናል፡፡ ያገለገሉትን ‹‹ወደ ጌታህ ደስታ ግባ!›› አላቸው ማለት ታማኝ አገልጋዮች መንግሥተ ሰማያትን ይወርሳሉና፡፡ ሰነፉ አገልጋይ ወደ ጨለማና ጥርስ ማፋጨት ወዳለበት ቦታ መወርወሩም ኀጥአን ወደ ሲኦል መግባታቸውን የሚያሳይ ነው፡፡

ከላይ ያነሳነው የቅዱስ ወንጌል ቃል፡- ‹‹ታማኝ አገልጋይ ማነው?›› ይላል፡፡ ይህ እያንዳንዱ በአርአያ እግዚአብሔር የተፈጠረ የሰው ልጅ ጥያቄ ነው፡፡ ለዚህ አምላካዊ ጥያቄ ምላሽ መስጠት ከሰው ልጆች ይጠበቃል፡፡ ከዚህ ቀጥለን በመጽሐፍ ቅዱስ ታሪካቸው ከተመዘገበላቸው ታማኝ አገልጋዮች መካከል ሦስቱን ጠቅሰን ከእነርሱ ሕይወት እንድንማር የሚያነሣሣ መጠነኛ ትምህርት እናቀርባለን፤

ሙሴ

ሊቀ ነቢያት ሙሴ ታማኝ አገልጋይ መኾኑን ቅዱሳት መጻሕፍት ይመሰክራሉ፤ ‹‹በመካከላችሁ ነቢይ ቢኖር እኔ እግዚአብሔር በራእይ እገለጥለታለሁ ወይም በሕልም አናግረዋለሁ፡፡ ባሪያዬ ሙሴ ግን እንዲህ አይደለም እርሱ በቤቴ ዅሉ የታመነ ነው፤›› እንዲል (ዘኍ.፲፪፥፮)፡፡ ይህ የፍጡር ቃል ሳይኾን በፈጣሪው የተሰጠ ምስክርነት ነው፡፡ በውኑ በዘመናችን እንኳን ፈጣሪ ፍጡራን ታማኝነቱን የሚመሰክሩለት አጋልጋይ ይኖር ይኾን? እንጃ! የሙሴን ታማኝ አገልጋይነት በረኃ፣ ስደት፣ መከራ፣ የፈርዖን ግርማ እና ቁጣ አልበገረውም፡፡ ዐርባ ዓመት ስለ ወንድሞቹ በመሰደድ ዐርባ ዓመት ደግሞ የተሰደደላቸው ወንድሞቹን በመምራት፣ ባሕር በመክፈል፣ ጠላት በመግደል፣ መና በማውረድ፣ ደመና በመጋረድ ውኃ ከዓለት አፍልቆ በማጠጣት መከራውን ከወገኖቹ ጋር በመቀበል የቀኑን ኃሩር፣ የሌሊቱን ቁር (ብርድ) ታግሦ በታማኝነት አገልግሏል፡፡ ታማኝነቱም እስከ ሞት ድረስ ነበር፡፡

‹‹ሙሴም ወደ እግዚብሔር ተመልሶወዮ እኒህ ሕዝብ ታላቅ ኃጢአት ሠርተዋል፡፡ ለራሳቸውም የወርቅ አማልክት አድርገዋል፡፡ አሁን ይህን ኀጢአታቸውን ይቅር በላቸው፤ ያለዚያ ግን ከጻፍከው መጽሐፍ እባክህ ደምስሰኝ? ከባለሟልነትህ አውጣኝ?›› ተብሎ ተጽፏል (ዘፀ.፴፪፥፴፩)፡፡ ታማኝ አገልጋይ የሚባለው እንደ ሙሴ ‹‹እኔ ልሙት ሌሎች ይዳኑ›› የሚል ሰው ነው፡፡ አሁን የምናየው ግን ፈጽሞ ከዚህ የተለየ ነው፡፡ ‹‹ሰዎች ይሙቱ፤ እኔ ልኑር፡፡ ሰዎች ጦም ይደሩ፤ እኔ ልብላ፡፡ ሰዎች ይራቆቱ፤ እኔ ልልበስ፡፡ ሰዎች ይዘኑ፤ እኔ ልደሰት›› ነው፡፡ ይህም ታማኝ አገልጋይ ያለ መኾን መገለጫ ነው፡፡ ታማኝ አገልጋይ ለሚያገለግላቸው ሰዎች ጥቅም ቅድሚያ የሚሰጥ እንጂ የራሱን ጥቅም የሚያስቀድም አይደለም፡፡

ዛሬ በዓለማችን የምንመለከተው ድርጊት ግን ‹‹ጩኸት ለአሞራ መብል ለጅግራ›› የሚባለውን ዓይነት ነው፡፡ በታማኝ አገልጋዮች ድካም የሚሸለሙ፤ ታማኝ አገልጋዮች በሠሩት ሪፖርት የሚያቀርቡ፤ ባልሠሩት ሥራ የሚወደሱ፤ ከጥቅሙ እንጂ ከድካሙ መካፈል የማይሹ ጥቂቶች አይደሉም፡፡ እንቅፋት የሚመታው እግርን ነው፡፡ አክሊል የሚቀዳጀው ግን ራስ ነው፡፡ ታማኝ አገልጋይ ማለት እንደራስ አክሊል ዘውድ የሚጸፋ ብቻ ሳይኾን እንደ እግር እንቅፋቱን፣ እሾኹን፣ ውጣ ውረዱን፣ መከራውንና ድካሙን የሚቀበል ነው፡፡ በጥቅም ጊዜ ለራሱ በአካፋ የሚዝቅ፤ ሌሎች በጭልፋ የሚቆነጥር አይደለም፡፡ ሙሴ ባሕር የከፈለው፣ መና ያወረደው ደመና የጋረደው ውኃ ያፈለቀው ለራሱ አልነበረም፤ ለሚመራቸው ሕዝብ ነበር እንጂ፡፡ ታማኝ አገልጋይ ያሰኘውም ይኸው ነው፡፡ በዚህ ከብሮበታል፤ ተመስግኖበታልም፡፡

ዳዊት

ነቢዩ ዳዊት ዘመነ መሳፍንት አልፎ ዘመነ ነገሥት ሲተካ እስራኤልን በንጉሥነት እንዲመራ እግዚአብሔር ከበግ ጥበቃ የመረጠው ንጉሥ ነው፡፡ እርሱም በተሰጠው ሥልጣን ሳይታበይ በታማኝነት ሕዝበ እስራኤልን መርቷል፡፡ እግዚአብሔር ለሙሴ እንደ መሰከረው ዅሉ ስለ ለዳዊትም መስክሮለታል፡፡ ‹‹እግዚአብሔር እንደ ልቡ የኾነ ሰው መርጧልናየዘይቱን ቀንድ ሞልተህ በልጆቹ መካከል ለእኔ ንጉሥ አዘጋጅቻለሁና ወደ እሴይ ወደ ቤተ ልሔም እልክሃለሁ፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (፩ሳሙ. ፲፫፥፲፫፤ ፲፮፥፪)፡፡

በመዝሙረ ዳዊትም ‹‹ወረከብክዎ ለዳዊት ገብርየ ወቀባዕክዎ ቅብዐ ቅዱስ፤ ባሪያዬ ዳዊትን አገኘሁት የተቀደሰ ዘይትንም ቀባሁት›› ተብሎ ተነግሮለታል (መዝ. ፹፰፥፳)፡፡ ይህንንም አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ በመጽሐፈ ሰዓታት ድርሰቱ፡- ‹‹ረከብክዎ ለዳዊት ገብርየ ብእሴ ምእመነ ዘከመ ልብየ፤ አገልጋዬ ዳዊትን እንደ ልቤ የታመነ ሰውን አገኘሁት›› ሲል ተርጕሞታል፡፡ ንጉሥ ዳዊት ከመንገሡ በፊት የተገኘው በታማኝነት ነበር፡፡ ከነገሠ በኋላም ታማኝ ነበር፡፡ አሁን በዚህ ዓለም የምንኖር እኛ ግን በድኅነት ታማኝ እንኾንና ሀብት፣ ሹመት፣ ሥልጣን ሲመጣ ታማኝነትን እናጣለን፤ እንዲያውም ታማኝነትን እንንቀዋለን፡፡ መስረቅ ጀግንነት ይመስለናል፡፡ መዋሸት ሥልጣኔ ይኾንልናል፡፡

ዳዊት ሳይሾም በጎቹን በመጠበቅ ታማኝ ነበር፡፡ በጎቹን የሚነጥቅ ተኩላ አንበሳ ቢመጣ በኋላው ተከትሎ ነብሩን በጡጫ፣ አንበሳውን በእርግጫ ብሎ በጎቹን ያስጥል ነበር፡፡ ‹‹እኔ ባሪያህ የአባቴን በጎች ስጠብቅ አንበሳ ወይም ድብ ይመጣ ነበር፡፡ ከመንጋውም ጠቦት ይወስድ ነበር፡፡ በኋላውም እከተለውና እመታው ነበር፤ ከአፉም አስጥለው ነበር፡፡ በተነሣብኝም ጊዜ ጉሮሮውን አንቄ እመታውና እገድለው ነበር፡፡ ይህም ፍልስጥኤማዊ ከነዚያ እንደ አንዱ ይኾናል፤ እንግዲህ እገድለው ዘንድ፤ ከእስራኤል ተግዳሮትን አስወግድ ዘንድ ዛሬ አልሔድምን? የሕያው አምላክ ጭፍሮችን ይገዳደር ዘንድ ይህ ቆላፍ ምንድን ነው? ከአንበሳና ከድብ ያስጣለኝ እግዚአብሔር ከዚህ ያልተገረዘ ፍልስጥኤማዊ እጅ ያስጥለኛል!›› በማለት እርሱ እንደ ተናገረው (፩ኛሳሙ.፲፯፥፴፬)፡፡

ዛሬም ቢኾን በእስራኤል ዘነፍስ በምእመናን ላይ የሚገዳደሩ ብዙ ፍልስኤማውያን ተሰልፈዋል፡፡ እነዚህን ድል የሚነሣ፤ በጎቹን ምእመናን ከተኩላ፣ ከአንበሳና፣ ከድብ አፍ የሚታደግ ታማኝ አገልጋይ ማነው? ከምእመናን ተግዳሮት የሚያርቅ ፈጣሪዬ ከመከራ ያድነኛል ብሎ የሚታመን የኢ አማንያን ብዛት የማያስፈራው ማን ነው? ከትንሽነቱ እስከ ታላቅነቱ የታመነ አገልጋይ ማነው? ለተሾመበት ሓላፊነት ታማኝ ማነው? አሁንም ዓለማችን ከሥጋውያን ባለ ሥልጣናትም ኾነ ከመንፈሳውያን መሪዎች የምትሻው ታማኝ ሰው ነው፡፡ በሙስና ያልተዘፈቀ፤ ጉቦ አይኑን ያላጨለመበት፤ ለመንጋው አርአያና ምሳሌ የሚኾን ሰው፤ ታማኝ አገልጋይ ማለት እርሱ ነው፡፡ በመሐላ የተቀበለውን የአገልግሎት ሓላፊነት የማይዘነጋ ጳጳስ፣ ቄስ፣ ዲያቆን፣ ሰባኪ፣ መምህር፣ ሐኪም፣ ዳኛ፣ ነጋዴ፣ ተማሪ፣ ወታደር፣ የቤት ሠራተኛ፣ የቢሮ ሠራተኛ ታማኝ መኾን አለበት፡፡

መንጋው በክህደት ሲጠፋ ዝም ብሎ የሚያይ ጳጳስ፣ ቄስ፣ ዲያቆን፣ መምህር፣ ሰባኪ፣ ታማኝ አይደለም፡፡ ታማሚው እየተሰቃየ የሚዝናና ሐኪም ታማኝ አይደለም፡፡ ፍርድ የሚያጎድል፤ ድሆችን የሚበድል፤ ለደሃ አደጎች የማይፈርድ ዳኛ ታማኝ አገልጋይ አይደለም፡፡ ቅቤ በሙዝ እና በድንች ቀላቅሎ፣ በርበሬ በሸክላ አፈር ጨምሮ፣ ሌሎችን አጭበርብሮ የሚሸጥ ነጋዴ ታማኝ አገልጋይ አይደለም፡፡ እየነገደ ያለው በሰው ሕይወት መኾኑን መዘንጋት የለበትም፡፡ ዅሉም እንደየአቅሙ በተሰጠው የአገልግሎት ዘርፍ ታማኝ መኾን አለበት፡፡

ዮሴፍ

ዮሴፍ ለወንድሞቹ ምግባቸውን ተሸክሞ የእርሱ ስንቅ ቢያልቅ የወንድሞቹን ስንቅ ያልበላ በትንሹ የታመነ ሰው ነበር፡፡ ወንድሞቹ ሸጠውት በቤተ ጲጥፋራ በሚያገለግልበት ጊዜም ታማኝ ነበር፡፡ ታማኝነቱ በጲጥፋራ ቤት ጌታ አድርጎታል፡፡ ‹‹ዮሴፍ ተሸጠአገልጋይም ኾነ፡፡ እግሮቹ በእግር ብረት ሰለሰሉ፡፡ ሰውነቱም ከብረት አመለጠች፡፡ ቃሉ ሳይደርስ የእግዚአብሔር ቃል ፈተነው፡፡ ንጉሥ ላከ፤ ፈታውም የሕዝብ አለቃ አድርጎ ሾመው፡፡ የቤቱም ጌታ አደረገው፡፡ በገንዘቡ ዅሉ ላይ ገዢ አደረገው፡፡ አለቆቹን እንደ እርሱ ይገሥፅ ዘንድ፤ ሽማግሌዎችን እንደ እርሱ ጥበበኞች ያደርጋቸው ዘንድ፤›› ተብሎ እንደ ተነገረለት (መዝ.፻፬፥፲፯)፡፡

በዚህ ኹኔታ የነበረው ዮሴፍ የጌታው ሚስት ሲወጣ ባቱን፣ ሲገባ ደረቱን እያየች ዐይኗን ጣለችበት፤ በዝሙት አይን ተመለከተችው፡፡ ‹‹ከእኔ ጋር ተኛ›› እያለችም በየቀኑ አስቸገረችው፡፡ እርሱ ግን ‹‹እምቢ›› አላት፡፡ ለጌታው ሚስትም፡- ‹‹እነሆ ጌታዬ በቤቱ ያለውን ዅሉ ለእኔ በእጄ አስረክቦኛል፡፡ በቤቱ ያለውን ምንም የሚያውቀው የለም፡፡ በዚህ ቤት ከእኔ የሚበልጥ ሰው የለም፡፡ ሚስቱ ስለ ኾንሽ ከአንቺ በቀር ያልሰጠኝ ነገር የለም፡፡ እንዴት ይህን ትልቅ ክፉ ነገር አደርጋለሁ? እንዴትስ በእግዚአብሔር ፊት ኀጢአትን እሠራለሁ?›› በማለት የዝሙት ጥያቄዋን ውድቅ አደረገባት (ዘፍ.፴፱፥፯)፡፡

በዮሴፍ ታማኝነት የጌታው ቤት ተባርኳል፡፡ ሀብቱ በዝቷል፡፡ በታማኝነቱ በቤቱ ያለውን ዅሉ ተረክቦ ነበር፡፡ የቀረበለት ፈተና ግን ከባድ ነበር፤ ኾኖም ግን በታማኝነቱ ለማለፍ ችሏል፡፡ ዮሴፍ በታማኝ አገልጋይነቱ በመጣበት መከራ ቢታሰርም እንኳን ያለ ሹመት አላደረም፤ የእስረኞች አለቃ ነበር፡፡ ከእስር ቤት ሲወጣም ግብጽን በሙሉ መርቷል፡፡ በግብጻውያን ላይ ተሾሟል፤ በጥቂቱ ታምኗልና፡፡ ‹‹በጥቂቱ የታመነ በብዙ ይሾማል›› እንዲል (ማቴ.፳፭፥፳፬)፡፡ዛሬ በእየአንዳንዱ ጓዳ እንደ እሳት የሚያቃጥሉ አገልጋዮች ናቸው ያሉት፡፡ ልጅ በፈላ ውኃ የሚቀቅሉ ናቸው የሚበዙት፡፡ እንኳን በዅሉ ገንዘብ ለመሾም በጥቃቅን ዕቃዎች እንኳን የሚታመን ሰው ጠፍቷል፡፡ ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ፡- ‹‹አቤቱ አድነኝ፤ ደግ ሰው አልቋልና፡፡ ከሰው ልጆችም መተማመን ጎድሏልና፤›› በማለት እንደ ተናገረው በመካከላችን መተማመን የለም (መዝ.፲፩፥፩)፡፡

እናም ከእነዚህ ሦስት ታማኝ አገልጋዮች (ሙሴ፣ ዳዊት እና ዮሴፍ) ሕይወት ዅሉም የሰው ልጅ ታማኝ አገልጋይነት የሚያሰጠውን ክብርና ጸጋ ተመልክቶ በታማኝነት ማገልገል ይገባዋል፡፡ ታማኝ መኾን መጀመሪያ የሚጠቅመው ራስን ነው፤ ከዚያ በኋላ ለአገር፣ ለወገን፣ ለቤተ ክርስቲያን፣ ላመኑትም ላላመኑትም ዅሉ ጠቃሚ ይኾናል፡፡ በመጨረሻም የጽድቅ አክሊልን ይቀዳጃል፤ መንግሥተ ሰማያትን ያወርሳል፡፡ ታማኝነት በሰውም፣ በእግዚአብሔርም ፊት ያስከብራልና፡፡ ጻድቃን፣ ሰማዕታት ቅዱሳን በታማኝነት በማገልገላቸው ፈጣሪአቸውን ደስ አሰኝተው ከብረዋል፡፡

በሓላፊው ገንዘብ ያልታመኑት እነይሁዳ፣ ሐናንያ እና ሰጲራ የደረሰባቸውን ጉዳት አይተናል፡፡ አካን ወልደ ከርሚንም ተመሳሳይ ቅጣት ደርሶበታል (ሐዋ.፭፥፩-፳፭)፡፡ ስለ ኾነም ዅሉም በተሰማራበት የአገልግሎት መስክ ታማኝ አገልጋይ ኾኖ ‹‹አንተ በጎ ታማኝ አገልጋይ በጥቂቱ ታምነሃል፤ በብዙ እሾምሀለሁ፤›› የሚለውን የጌታውን የምስጋና ቃል ለመስማት ተዘጋጅቶ መጠበቅ ይገባዋል፡፡ መልካም አገልግሎት አገልግለን፣ በእግዚአብሔር ‹አግብርት ኄራን፤ ታማኝ አገልጋዮች› እንድንባል፤ መንግሥቱንም እንድንወርስ አምላካችን ይርዳን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

በእንተ ጾም

በዲያቆን ዘአማኑኤል አንተነህ

መጋቢት ፲፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ጾም ‹‹ጾመ›› ከሚለው የግእዝ ግስ የተገኘ ሲኾን ትርጕሙም መተው፣ መጠበቅ፣ መከልከል ማለት ነው፡፡ ጾም ከምግብ መከልከል ብቻ ሳይኾን ከክፉ ተግባር ዅሉ መቆጠብ ጭምር ነው፡፡ ሠለስቱ ምዕትም፡- ‹‹ጾምሰ ተከልኦተ ብእሲ እመብልዕ በጊዜ ዕውቅ በውስተ ሕግ፤ ጾምስ በታወቀው ሰዓት፣ በታወቀው ዕለት ሰው ከምግብ የሚከለከለው መከልከል ነው›› በማለት የጾምን ትርጕም ያስረዳሉ /ፍትሐ ነገሥት፣ አንቀጽ ፲፭/፡፡

ጾም በብሉይ ኪዳንም ኾነ በሐዲስ ኪዳን የታወቀ፣ በነቢያት የነበረ፣ በክርስቶስ የጸና፣ በሐዋርያት የተሰበከ እና የተረጋገጠ መንፈሳዊ ሕግ፤ ፈጣሪን መለመኛ መንፈሳዊ መሣሪያ ነው፡፡ ጾም ሰው ሠራሽ ሕግ ሳይኾን ልዑል እግዚአብሔር የመሠረተው፣ ከእግዚአብሔር ለሰው ልጅ የተሰጠ የመጀመሪያው ትእዛዝ ነው፡፡ ጌታችን መድኀኒችን ኢየሱስ ክርስቶስም እከብር አይል ክቡር፣ እነግሥ አይል ንጉሥ፣ እጸድቅ አይል ጽድቅ የባሕርዩ የኾነ አምላክ ነው፡፡ ለእኛ አርአያ ቤዛ ሊኾነን፣ እናንተም ብትጾሙ ብትጸልዩ አጋንንትን ድል ትነሳላችሁ ሲለን፣ ጾምን ለመባረክ ለመቀደስ፤ በመብል ምክንያት ስተን ስለ ነበር ስለ እኛ ኀጢአት እና በደል ሲል ዐርባ ቀንና ሌሊት ጾሟል፡፡

ጌታችን ሲጾም ዐርባውን መዓልት እና ሌሊት ሙሉ ምንም እኽል ውኃ አልቀመሰም፡፡ ሊቀ ነቢያት ሙሴም እንደዚሁ ጽላተ ሕጉን ከእግዚአብሔር ሲቀበል እኽል ውኃ አልቀመሰም ነበር፡፡ ምክንያቱም አምላካችን ‹‹በእኔ የሚያምን እኔ የማደርገውን ያደርጋል፤ ከእኔ የበለጠም ያደርጋል›› ብሏልና፡፡ አባቶቻችን ጻድቃንም ከዐሥረኛው ማዕረግ (ከዊነ እሳት) ላይ ሲደርሱ በእርሱ መንፈስ (በመንፈስ ቅዱስ) ኃይል ታግዘው ከእኽል ውኃ ተከልክለው ይጾማሉ፡፡ ይህም በሥጋዊ ዓይን ሲመዘን ፈጽሞ የሚከብድ ነው፡፡ ሃይማኖት ከሳይንስና ከአእምሮ በላይ ነውና፡፡ በዚህም  ሃይማኖት የሚቀበሉት እንጅ የሚጠራጠሩት የሚፈላሰፉት እንዳልኾነ እንረዳለን፡፡

የጾም ሥርዓት

መጽሐፍ ‹‹ተሰአሎ ለአቡከ ወይነግረከ፤ አባትህን ጠይቅ፤ ይነግርህማል፤›› /ዘዳ.፴፪፥፯/ እንዳለ ጾም እንዴት እንደሚጾም አባቶችን መጠየቅ እና የአባቶችን ፈለግ መከተል ያስፈልጋል፡፡ ቅዱስ  ኤጲፋንዮስ ‹‹ቤተ ክርስቲያን እናቱ ያልኾነች ሰው እግዚአብሔር አባቱ አይኾነውም›› በማለት እንደ ተናገረው ያለ ቤተ ክርስቲያን እግዚአብሔርን፤ ያለ እግዚአብሔር ደግሞ ቤተ ክርስቲያንን ማወቅ አይቻልም፡፡ ስለዚህ ዘወትር ወደ ቤተ ክርስቲያን እየሔዱ ቃለ እግዚአብሔር መማር፣ መጸለይ፣ ሥጋውን ደሙን መቀበል መገስገስ ክርስቲያናዊ ግዴታ ነው፡፡ ‹‹ቤተ ክርስቲያን ለክርስቲያን›› እንዲሉ አበው፡፡ በጾም ወቅት ደግሞ ይህንን ተግባር ይበልጥ ማሳደግ ይገባል፡፡

በጾም ወቅት የሥጋ አለቃ ነፍስ ናት፡፡ ነፍስ ፈላጭ፣ ቆራጭ፣ አዛዥ ናት፡፡ ሰው መልካም ሥራ ከሠራ በነፍስ በሥጋው ይቀደሳል፤ ገነት (መንግሥተ ሰማያትን) ይወርሳል፡፡ ክፉ ከሠራ ደግሞ በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስን ያጣል፤ ወደ ሲኦል (ገሃነመ እሳት) ይወርዳል፡፡ ሰው ኀጢአተኛ ነው ሲባል ፈቃደ ሥጋው ሠልጥኖበታል ማለት ነው፡፡ ጻድቅ  ነው ሲባል  ደግሞ ፈቃደ ሥጋውን አሸንፏል (ለፈቃደ ነፍሱ እንዲገዛ አድርጓል) ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ሰው ሲቀደስም፣ ሲረክስም የሚኖረው በፈቃደ ሥጋ እና ፈቃደ ነፍስ መካከል ባለው የአሸናፊነትና ተሸናፊነት ትግል ነው፡፡

ጾም ራስን ዝቅ የማድረግ፣ የጸሎት እና የንስሐ ጊዜ እንደኾነ ቅዱሳት መጻሕፍት ይነግሩናል፡፡ /ዕዝ. ፰፥፳፩፤ ነህ. ፩፥፬፤ ዳን.፱፥፫/፡፡ ስለዚህም ራሳችንን ዝቅ በማድረግ (በትሕትና) መጾም ይገባናል፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስ በምዕራፍ ፶፰ ቍጥር ፭ ላይ ‹‹እኔ የመረጥኩት ጾም ይህ ነውን? ሰውስ ነፍሱን የሚያዋርደው እንደዚህ ባለ ቀን ነውን? በውኑ ራሱን እንደ እንግጫ ዝቅ ያደርግ ዘንድ ማቅንና አመድንም በበታቹ ያነጥፍ ዘንድ ነውን?›› ይላል፡፡ እንግጫ ማለት ባሕር ውስጥ የሚበቅል ሣር ነው፡፡ በቀዳም ሥዑር ካህናት ‹‹ጌታ ተመረመረ፤ ዲያብሎስ ታሰረ፤›› እያሉ ለደስታ መግለጫ የሚሰጡት እና ራስ ላይ የሚታሰር ለምለም ሣር ነው፡፡ እንግጫ (ግጫ – በአንዳንድ አካባቢዎች) ሲያድግ ራሱን ዝቅ ያደርጋል፤ እያደገ ሲሔድ ራሱን ይደፋል (ዝቅ ያደርጋል)፡፡

ነቢዩ ኢሳይያስ ራሳችሁን እንደ እንግጫ (ግጫ) ዝቅ አድርጉ ማለቱ  በጾም ወቅት ‹‹እንደዚህ ነው የምጾመው፤ እስከዚህ ሰዓት ድረስ ነው የምጾመው›› እያልን ውዳሴ ከንቱን መሻት የለብንም ሲል ነው፡፡ ሰው እያወቀ ሲሔድ ራሱን ይደብቃል እንጅ ራሱን ከፍ ከፍ አያደርግም፡፡ የጾም ወቅት ትሕትናን ገንዘብ የምናደርግበትና ይበልጥ የምናሳድግበት ወቅት ነው፡፡ አንድ ክርስቲያን ፈተናን ችሎ በትዕግሥት የሚያሳልፍ፣ እየሰማ የሚተው መኾን አለበት፡፡ ነቢዩ ዕዝራም በመጽሐፈ ዕዝራ ፰፥፳፩ ላይ ‹‹በአምላካችን ፊት ራሳችንን እናዋርድ ዘንድ ከእርሱም የቀናውን መንገድ ለእኛ እና ለልጆቻችን ለንብረታችንም ሁሉ እንለምን ዘንድ በዚያ በአኅዋ ወንዝ አጠገብ ጾም አወጅሁ›› በማለት ራስን ዝቅ በማድረግ ለአምላክ ፈቃድ መገዛት እንደሚገባ ያስተምረናል፡፡

የጾም ሰዓት

ስለ ጾም ሲነገር የጾም ሰዓትም አብሮ ይነሣል፡፡ በዘፈቀደ ሳይኾን በሰዓት የተወሰነ ጾም መጾም እንደሚገባን መጽሐፍ ቅዱስ ያስረዳናል፡፡ ‹‹የእስራኤልም ልጆች ዅሉ ሕዝቡም ዅሉ ወጥተው ወደ ቤቴል መጡ፤ አለቀሱም፡፡ በዚያም በእግዚአብሔር ፊት ተቀመጡ፡፡ በዚያም ቀን እስከ ማታ ድረስ ጾሙ፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ /መሳ.፳፥፳፮/፡፡ የጾም ሰዓትም በፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፲፭ ተዘረዝሯል፡፡ ሠለስቱ ምዕት ‹‹ቢቻላችሁ ከዚህ አብዝታችሁ ጹሙ›› እንደዚሁም ‹‹በጾም ምክንያት ጠብ ክርክር ቢኾን መጾም ይገባል፤ ከመብላት መጾም ይሻላልና፤›› በማለት ከተወሰነው ሰዓት በላይ አብልጦ መጾም እንደሚቻልና ከመብል ይልቅ ለጾም ማድላት እንደሚገባ ነግረውናል /ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፲፭ ቍጥር ፭፻፹፬/፡፡

ሰው ይረባኛል ይጠቅመኛል ብሎ አብዝቶ ከመጾሙ የተነሣ መላእክትን፣ አባ እንጦንስና አባ መቃርስን እንደሚመስል ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ያስተምራሉ፡፡ አምላካችን ‹‹እናንተን የሚቀበል እኔን ይቀበላል›› የሚል ቃል ኪዳን የሰጣቸው አባቶቻችን መምህራን የምንጾማቸውን አጽዋማት እና የምንጾምበትን የሰዓት ጊዜ ወስነውልናል፡፡ በቅዱሳን አባቶቻችን ላይ አድሮ ሥርዓቱን የሠራልን ራሱ እግዚአብሔር ነው፡፡ ምክንያቱም ካለ እርሱ ፈቃድ እጽፍ፣ እተረጕም ቢሉ አይቻልምና፡፡ ጌታችን በወንጌሉ ‹‹ጌታ ሆይ ጌታ ሆይ የሚለኝ ዅሉ ወደ መንግሥተ ሰማያት የሚገባ አይደለም፤ ትእዛዜን የሚያከብር እንጅ፤›› እንዳለ በመንፈስ ቅዱስ ኀይል ተመርተው አባቶች  የደነገጉትን ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ማክበር እና መጠበቅ አለብን፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹በየጥቂቱ ማደግ ይገባል›› እንዳለው ዅሉንም ነገር በአቅም ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ ጾምን ስንጾምም አቅምን ማወቅም ተገቢ ነው፡፡ ብዙ ለመጾም ስንወስን ጽናታችንና ልምዳችንን ግምት ውስጥ በማስገባት መኾን ይኖርበታል፡፡ ካለበለዚያ ጥብዓት ጎድሎን፣ ትዕግሥት አንሶን እግዚአብሔርን ልናማርር እንችላለን፡፡ ጾመን የማናውቅ ሰዎች በስሜት ተነሣሥተን በአንድ ጊዜ ቀኑን ሙሉ መጾም አለብን ማለት የለብንም፡፡ ክርስትና የስሜት ጉዞ አይደለምና፡፡ እስከ ሰባት ሰዓት ጹሞ የማያውቅ ክርስቲያን እስከ ዐሥራ ሦስት ሊጾም አይችልም፡፡ በስሜት የሚደረግ ማንኛውም ነገር ፍጻሜ አይኖረውምና ስንጾም አቅማችንን ማወቅ ተገቢ ነው፤ ለዚህ ደግሞ ከንስሐ አባት ጋር መመካከር ይጠቅማል፡፡

ጠቢቡ ሰሎሞን ‹‹እጅግም ድሀ አታድርገኝ፤ እጅግም ሀብት አትስጠኝ›› ይላል፡፡ እኛም ስንጾምም ስንለምንም በአቅማችን መኾን አለበት፡፡ ስለጾምና የሰዓት ገደብ ሲነገር ማስተዋል የሚገባን ቁም ነገር ከእኽል ውኃ ከመከልከል አኳያ ጾም በቍጥርና በጊዜ የተወሰነ ይኹን እንጂ ከክፉ ተግባር ከመራቅ አንጻር ክርስቲያን እስኪሞት ድረስ ጾመኛ ነው፡፡ ምንጊዜም ቢኾን ከክፉ ነገር፣ ከኀጢአት ዅሉ መጾም (መከልከል) ይጠበቅበታልና፡፡ ዅላችንም ይህን ክርስቲያናዊ ሓላፊነት መዘንጋት የለብንም፡፡ ከዚህ ላይ ግን አንድ ሰው በመጾሙ ብቻ አምላክን ያስደስተዋል ማለት አይደለም፡፡ መጾም ያለበትም ለሥራው ኀጢአት ማካካሻ አይደለም፡፡ የኀጢአት ስርየት የሚገኘው ንስሐ በመግባት እንጅ በመጾም ብቻ አይደለምና፡፡ ሌሎችንም የትሩፋት ምግባራት መሥራት ስንችል ነው ኀጢአታችን የሚሰርይልን፡፡ ስለዚህ ራሳችንን ዝቅ በማድረግ፣ ንስሐ በመግባት፣ በመጸለይ፣ በመመጽወት ከጾምን ኀጢአታችን ይሰረይልናል ማለት ነው ‹‹በጾም ወበጸሎት ይሰረይ ኵሉ ኃጢአት፤ በጾም በጸሎት ኀጢአት ዅሉ ይደመሰሳል፤›› እንዲሉ ሊቃውንት፡፡

ጾም እና ፈተና

‹‹ቤተ ክርስቲያን እየሔድኹ፣ እየጾምኹ፣ እየጸለይኹ፣ እፈተናለሁ፤ ለምንድን ነው?›› የምንል ብዙዎች ነን፡፡ ወደ ቤተ ክርስቲያን ስሔድ ፈተና እየበዛብኝ ነው በማለት ከቤቱ የምንርቅም ጥቂቶች አይደለንም፡፡ ብዙ ጊዜ ከመልካም ነገር በስተጀርባ ፈተና አለ፡፡ ከጌታችን የምንማረው ሕይወትም ይኸን ነው፡፡ የማይሾሙት ንጉሥ፣ የማያበድሩት ባለጠጋ፣ ዅሉን የፈጠረ፣ ዅሉን የሚገዛ ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለእኛ ሲል ጾመ፤ ተራበ፤ በሰይጣን ተፈተነ፡፡ በእኛ ላይም ብዙ ፈተና ቢመጣብን ለምን ያስደንቃል? ቅዱስ ዳዊት ‹‹ነፍሴን በጾም አስመረርኋት፤ ለስድብም ኾነብኝ›› ይላል /መዝ.፷፱፥፲/፡፡ በክርስትና ሕይወቱ የሚበረታ ሰው ይሰደዳል፤ ይሸነገላል፤ ፈተና ይበዛበታል፡፡ በዚህ ጊዜ ‹‹ለሚያሳድዱህ ጹምላቸው›› በማለት ቅዱሳን ሐዋርያት እንዳዘዙን ለሚያሳድዱን መጾም መጸለይ ይኖርብናል /ዲድስቅልያ ፩፥፭/፡፡ ክርስትና ሲገፉ መግፋት አይደለምና፡፡ በረከታቸው ይደርብንና ብፁዕ አቡነ በርናባስ ‹‹ከቤተ ክርስቲያንን የተጠጋ እንኳን ሰው ዛፉ ይለመልማል›› ይሉ ነበር፡፡ እግዚአብሔር አባታችን፣ ቤተ ክርስቲያን እናታችን ብሎ የሚኖር ሰው ፈተና በየጊዜው ቢገጥመውም መጨረሻው ያማረ ነው፡፡ እግዚአብሔርን ተከትሎ የወደቀ የለምና፡፡

የጾም ጥቅም

በቅዱሳት መጻሕፍት እንደ ተገለጸው ጾም የሚከተሉት ጥቅሞች አሉት፤

  • የሥጋን ምኞት ያጠፋል፤
  • የነፍስ ቍስልን ያደርቃል፤
  • ፈቃደ ሥጋን ለፈቃደ ነፍስ ያስገዛል /ፍት.ነገ.፲፭፥፭፻፷፬/፤
  • መላእክትን መስሎ ለመኖር ያስችላል፤
  • ልዩ ልዩ መከራን ያቃልላል፤
  • አጋንንትን ያስወጣል /ኢያ.፯፥፮-፱/፤
  • ሰማያዊ ክብር እና ጸጋን ያስገኛል /ኛነገ.፲፱፥፰/፤
  • በመንግሥተ ሰማያት ለመኖር የሚያስችል ምግባርን ያሠራል /ሉቃ.፮፥፳፩/፤
  • ከእግዚአብሔር ዘንድ ይቅርታ እና ምሕረትን ለማግኘት ይረዳል፤
  • አጋንንትና ጠላትን ድል ለማድረግ ያግዛል /ማቴ.፬፥፲፩፤ መጽሐፈ አስቴር ምዕ.፯/፤
  • ፈቃደ እግዚአብሔርን ለመፈጸም ይረዳል /፩ኛነገ.፲፱፥፩/፤
  • ከእግዚአብሔር ቍጣ ለመዳን ያስችላል /ዮናስ ፫፥፩/፤
  • የተደበቀ ምሥጢርን ይገልጣል /ዳን.፲፥፲፬/፤
  • ጸጥታን እና ርጋታን ያስተምራል፤
  • ከቅዱሳን በረከት ያሳትፋል፤
  • ሕይወትን ያድሳል፤
  • መንፈሳዊ ኃይልን ያሰጣል /፩ኛሳሙ.፯፥፭/፤ጥበብን ይገልጣል /ዕዝራ ፯፥፮፤ ዳን.፱፥፪/፤
  • ክህደት ጥርጥርን በማጥፋት እምነትን ለማጠንከር ይረዳል፤
  • ዕድሜን ያረዝማል፤
  • ትዕግሥትን ያስተምራል፤
  • በመላእክት ጠባቂነት ለመኖር ያስችላል /ዘፀ.፲፬፥፲፱. ሐዋ.፲፥፫/፡፡

ጾም ከሚያስገኘው መንሳዊ ጸጋና በረከት ባሻገር በርካታ ሥጋውያን ጥቅሞችም እንዳሉት በጾም ዙሪያ የተደረጉ ልዩ ልዩ ሳይንሳዊ ጥናቶች ያሳያሉ፡፡ በጥናቶቹ መሠረትም ጾም፡-

  • የደምና የስኳር መጠንን ይቆጣጠራል፤
  • የአንጎል እንቅስቃሴ የተቀላጠፈ እንዲኾን ያደርጋል፤
  • የስብ ክምችትን ይቀንሳል፤
  • የምግብ መፍጨት ስርዓታችንን ያስተካክላል፤
  • የካንሰር ሕዋሳት ዕድገትን ይከላከላል፤
  • የጠራ የሰውነት ቆዳ እንዲኖረን ያደርጋል፤
  • በሽታ የመከላከል አቅምን ይጨምራል፡፡

በአጠቃላይ ጾም ሰው ሠራሽ ሕግ አይደለም፤ የመሠረተውም ራሱ ልዑል እግዚአብሔር ነው፡፡ አምላካችን አዳምና ሔዋንን ‹‹ዕፀ በለስን አትብሉ›› ብሎ ባዘዛቸው ጊዜ የጾም ሕግን ሠርቶልናል፡፡ በዚህም ጾም የመጀመሪያ ትእዛዝ ናት እንላለን፡፡ አዳም በመብል ምክንያት ሕገ እግዚአብሔርን በመጣሱ ነው ከክብሩ የወረደው፡፡ እኛም ብንጾም እንጠቀማለን፤ ባንጾም ደግሞ በረከትን እናጣለን፡፡ ቅዱስ ዳዊት ‹‹ሥጋዬ ቅቤ በማጣት ከሳ፤›› /መዝ.፻፱፥፳፬/፤ ነቢዩ ዳንኤልም ‹‹ማለፊያ እንጀራም አልበላሁም፤ ሥጋ እና ጠጅም በአፌ አልገባም፤›› /ዳን.፲፥፫/ ሲሉ እንደ ተናገሩት፣ በጾም ወቅት ከጥሉላት ምግቦች መከልከል አለብን፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹መብል ግን ወደ እግዚአብሔር አያቀርበንም፤ ባንበላም ምንም አይጎድለንም ብንበላም ምንም አይተርፈንም፤›› ሲል ማስተማሩም ከመብል ተከልክለን መጾማችን ወደ እግዚአብሔር የምንቀርብበት መንገድ መኾኑን ያመላክታል /ሮሜ.፲፬፥፯፤ ፩ኛቆሮ.፰፥፰/፡፡ አበው ‹‹ጾም ገድፎ የወፈረ በዓል ሽሮ የከበረ የለም›› እንደሚሉት በጾም ወቅት በልተን ከምናገኘው ጥቅም ይልቅ ጾመን ከእግዚአብሔር ዘንድ የምንቀበለው በረከት ይበልጣል፡፡

ጾም ቍስለ ነፍስን የምትፈውስ፣ ኃይለ ፍትወትን የምታደክም፣ የበጎ ምግባራት ዅሉ መጀመሪያ፣ ጸጋ እግዚአብሔርን የምታሰጥ፣ ለጽሙዳን ክብራቸው፣ ለደናግል የንጽሕና ጌጣቸው፣ የጸሎት እናት፣ የዕንባ መገኛ ምንጭ፣ አርምሞን የምታስተምር፣ ለበጎ ሥራ ዅሉ የምታነቃቃ፣ ሰውነትን በእግዚአብሔር ፊት በማዋረድ ትሕትናን ገንዘብ ለማድረግ የምትረዳ መድኃኒተ ነፍስ ናት /ማር ይስሐቅ አንቀጽ ፬ ምዕራፍ ፮/፡፡ እንደዚሁም ጾም ዕድሜን ያረዝማል፡፡ በጾም በጸሎት ተወስነው፣ ረጅም ዕድሜ የኖሩ አባቶቻችን ሕይወትም ለዚህ ማስረጃ ነው፡፡ ለምሳሌ ቅዱስ ቄርሎስ ዘአንኮራይት ፻፰፤ ቅዱስ እንጦንስ ፻፭፤ ቅዱስ መቃርስ ዘእስክንድርያ ፻ ዓመት በምድር ላይ ቆይተዋል፡፡ ምእመናንም ጾምን ስንጾም አምላካችን ዕድሜአችንን ለንስሐ ያረዝምልናል፡፡ በጾም ወቅት መጸለይ፣ መመጽወት፣ መስገድ በጾም የምናገኘውን ዋጋ ከፍ ያደርገዋል፡፡ ‹‹ስለ ኀጢአቱ እንደሚጾም፣ እንደሚጸልይ ሰው ኹኑ›› እንዳለ ቅዱስ ያሬድ፡፡

አንድ ክርስቲያን ጾም አልጾምም የማለት ሃይማኖታዊ ሥልጣን የለውም፡፡ ምክንያቱም ጾም ለዅሉም ክርስቲያን ሕግ ኾኖ የተሰጠ የአምላክ ትእዛዝ ነውና፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ኢዩኤል ‹‹ጾምን ቀድሱ፤ ጉባኤውንም አውጁ፤›› በማለት መጾም፣ መጸለይ ክርስቲያናዊ ግዴታ መኾኑን ነግሮናል /ኢዩ.፪፥፲፭/፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም ‹‹አገልግሎታችን እንዳይነቀፍ በአንዳች ነገር ማሰናከያ ከቶ አንሰጥም›› ሲል ምክንያት እየፈጠርን ከመንፈሳዊ ሕይወትና ከአገልግሎት ወደ ኋላ ማለት እንደሌለብን አስተምሮናል /፪ኛቆሮ.፮፥፫/፡፡ ብፁዕ አቡነ ሺኖዳ ‹‹በዐቢይ ጾም ሕይወቱን ያልቀየረ ክርስቲያን በሌሎች አጽዋማት ይቀይራል ለማለት ይከብዳል›› ይላሉ፡፡ እንደሚታወቀው በዐቢይ ጾም ከበሮ እና ጸናጽል ዅሉ ይጾማሉ፡፡ ይኸውም የጾሙን ትልቅነት ያረጋግጥልናል፡፡ የዜማ መሣሪያዎች ዐቢይ ጾምን ከጾሙ ለባዊነት ያለን የሰው ልጆችስ (ክርስቲያኖች) ለጾሙ ምን ያህል ዋጋ እንሰጥ ይኾን? ዅላችንም ጾሙን በደስታና በፍቅር ጾመን በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስን እናገኝ ዘንድ የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት፣ የቅዱሳን ተራዳዒነት አይለየን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የዐቢይ ጾም ሳምንታት

በመምህር ምሥጢረ ሥላሴ ማናየ

መጋቢት ፲፩ ቀን ፳፻፱ .

ዘወረደ

ትርጕሙ ‹ከሰማየ ሰማያት የወረደ› ማለት ነው፡፡ ከሰማየ ሰማያት የወረደውን፣ ከድንግል ማርያም የተወለደውን በጥንት ስሙ ወልድ፣ ቃል በኋላ ስሙ ኢየሱስ ክርስቶስ፣ አማኑኤል የተባለውን ሰው የኾነውን አምላክ ለማመስገን ርደቱን (ከሰማየ ሰማያት መውረዱን) ለመዘከር የሚጾም ጾም ነው፡፡ ጌታችን ጾመ ከማለት አስቀድሞ ከሰማየ ሰማያት መውረዱን ከድንግል ማርያም መወለዱን መናገር አስፈላጊ ነውና የመጀመሪያው ሳምንት ‹ዘወረደ› ተብሏል፡፡ ‹‹አንተ በሰማይ ወአንተ በምድር ወአንተ በባሕር ወአንተ በየብስ፤ አንተ በሰማይ አለህ፤ በምድር በባሕርም በየብስም አለህ፤›› የተባለውን በሰማይ በምድር ምሉዕ የኾነውን አምላክ ‹ወረደ፤ መጣ› ብሎ መናገር ‹ሰው ኾነ› ማለት ነው፡፡ ሰው ኾኖ መገለጡን ለማስረዳት ነው እንጂ መውረድ መውጣት የሚባሉ ቃላት በዅሉ ምሉዕ ለኾነው መለኮት አይስማሙትም፡፡ ቃላቱ ሰውኛ አነጋገርን የሚያመለክቱ ናቸውና፡፡ መተርጕማን አበው ‹‹‹ዘወረደ› ማለት ‹ሰው የኾነ› ማለት ነው›› ብለው ይተረጕማሉ፡፡ አምላካችን ሰው ከኾነ በኋላ ‹መጣ፤ ሔደ፤ ወረደ፤ ዐረገ› የሚሉ ቃላት ይስማሙታል፡፡ ምልዓቱን ሳይለቅ በሰው አካል ተወስኖ ታይቷልና፡፡ ስለዚህ ‹ወረደ› እግዚአብሔር ሰው ኾኖ መገለጡን፤ ‹ዐረገ› ደግሞ የሰውነቱን ሥራ መፈጸሙን ያሳያል፡፡ ዐረገ ስንልም ቀድሞ በሰማይ የለም ለማለት አይደለም፤ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመለኮቱ በዓለሙ ዅሉ ምሉዕ ነውና፡፡

ጾሙን ሐዋርያት፣ ስያሜውንና የምስጋናውን ሥርዓት ቅዱስ ያሬድ አዘጋጅተዋል፡፡ ቅዱስ ያሬድ ነቢያትን በንባብ፤ ሐዋርያትን በስብከት፤ ሊቃውንትን በትርጓሜ፤ መላእክትን በዜማ ይመስላቸዋል፡፡ ቅዱስ ያሬድ የመላእክትን የምስጋና ሥርዓት ወደ ምድር አምጥቷል፡፡ የነቢያትን ትንቢት፣ የሐዋርያትን ትምህርት በሚገባ ተርጒሞ፣ አብራርቶ፣ አመሥጥሮ አዘጋጅቶታል፡፡ ሐዋርያት ጾሙን ጾመው የጾም ሕግ ደንግገዋል፤ ቅዱስ ያሬድም ለጾሙ ስያሜ ሰጥቶ ምስጋና ከነሥርዓቱ አዘጋጅቶ አቅርቧል፡፡ቤተ ክርስቲያናችንም የመጀመሪያው የዐቢይ ጾም ሳምንትን (ዘወረደን) ስያሜ እንደ ቅዱስ ያሬድ ከሐዋርያት ተቀብላ ታስተምራለች፡፡ ይህ የመጀመሪያው ሳምንት ‹ጾመ ሕርቃል› እየተባለም ይጠራል፡፡ ሕርቃል (ኤራቅሊዮስ) በ፮፻፲፬ ዓ.ም የነበረ የቤዛንታይን ንጉሥ ነው፡፡ ለክርስቲያኖች ባደረገው ርዳታ ምክንያት አንድ ሳምንት ጾመውለት ነበር፡፡ ያላወቁ ‹ጾመ ሕርቃል› ብለው አንድ ጊዜ ጾመው ትተውታል፡፡ ጥንቱን የቅዱሳን ሐዋርያት መኾኑን ያወቁ ምእመናን ግን ዅልጊዜ በየዓመቱ ይጾሙት ነበር፡፡ ዛሬም ድረስ ጾመ ሕርቃል እየተባለ ይጠራል፡፡ ሙሉ ታሪኩ በፍትሐ ነገሥት ትርጓሜ አንቀጽ ፲፭ ላይ ይገኛል፡፡

ቅድስት

‹ቅድስት› ማለት ‹የተለየች፣ የነጻች፣ የከበረች› ማለት ነው፡፡ ይኸውም ጌታችን ጾም የጀመረባት፣ ልዩ፤ የተቀደሰች፤ የከበረች፤ ልዩ፣ ንጹሕ፣ ክቡር በሚኾን በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተጾመች መኾኗን ያመላክታል፡፡ ይህች ጾም በማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ አራት የተገለጠችው የጌታችን ጾም ስትኾን፣ ስያሜዋና የዕለቷ የምስጋና ሥርዓትም የቅዱስ ያሬድ ነው፡፡ አምላካችን በገዳመ ቆሮንቶስ ዐርባ መዓልትና ዐርባ ሌሊት በጾመበት ጊዜያት እነዚህ ሦስቱን አርእስተ ኃጣውእ ድል አድርጓል፡፡ ሦስቱ አርእስተ ኃጣውእ የሚባሉትም፡- ትዕቢት፣ ስስትና ፍቅረ ንዋይ ናቸው፡፡ በእነዚህ ሦስት ኃጢአቶች ጌታችን በዲያሎስ በተፈተነ ጊዜ በትዕቢት ቢመጣበት በትሕትና፤ በስስት ቢመጣበት በትዕግሥት፤ በፍቅረ ንዋይ ቢመጣባት በጸሊዓ ንዋይ ጌታችን ዲያሎስን ድል አድርጎታል፡፡ ለእኛም እነዚህን ድል ለማድረግ የምንችልበትን ጥበብ – ጾምን ገልጦልናል፡፡ ትዕቢት ያልተሰጠንን መሻት፣ ስስት አልጠግብ ባይነት ስግብግብ መኾን፣ ፍቅረ ንዋይ ለገንዘብ ሲሉ ፈጣሪን መካድ ነው፡፡ አንደ ክርስቲያን ሦስቱን አርእስተ ኃጣውእ ድል ካደረገ ሌሎችን ኃጣውእ በቀላሉ ድል ማድረግ ይቻለዋል፡፡

ምኵራብ

ሦስተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ‹ምኵራብ› ይባላል፡፡ ምኵራብ አምልኮተ እግዚአብሔር ሲፈጸምበት፣ ሕገ ኦሪት ሲነበብበት የነበረ በአይሁድ የሚሠራ መካነ ጸሎት ነው፡፡ ዘወትር ቅዳሜ ብዙ ሕዝብ ይሰበሰብበት ስለ ነበር ጌታችን ለማስተማር ብዙ ጊዜ በምኵራብ ተገኝቶአል፡፡ ስያሜው የተወሰደው በዮሐንስ ፪፥፲፬ ‹‹ወረከበ በምኵራብ እለ ይሠይጡ አልህምተ ወአባግዐ ወአርጋበ …፤ በመቅደስም በሬዎችን፣ ላሞችን፣ በጎችን፣ ርግቦችን፣ የሚሸጡትን አገኘ …›› ተብሎ ከተገለጸው ኃይለ ቃል ላይ ሲኾን፣ ‹ምኵራብ› የሚለው ቃልም በአማርኛ ‹መቅደስ› ተብሎ ተተርጕሟል፡፡ ምኵራብ የሚባለው ሳምንት ጌታችን ወደ ምኵራብ ገብቶ ማስተማሩ የሚነገርበት፤ ‹‹ቤቴ የጸሎት ቤት ይባላል፤ እናንተ ግን የሌቦች ዋሻ አደረጋችሁት›› ብሎ በምኵራብ ይሸጡ፣ ይለውጡ የነበሩትን የገሠፀበት፤ ቤተ መቅደስን የከብት መንጃ የወርቅና የብር መነገጃ ያደረጉ ሰዎችን ከነሸቀጣቸው ከቤተ መቅደስ ያስወጣበት፤ ቤተ መቅደስ የእግዚአብሔር ማደሪያ፣ የስሙ መጠሪያ፣ የጸሎት ሥፍራ መኾኗን ያስረዳበትና ያወጀበት፤ በቤተ መቅደስ የንግድ ሥራ ማከናወን እንደማይገባ ያረጋገጠበት ዕለት ነው፡፡

መጻጒዕ

አራተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ‹መጻጒዕ› ይባላል፡፡ ስያሜው በዮሐንስ ወንጌል ፭፥፩ ላይ ከሚገኘው ኃይለ ቃል የተወሰደ ነው፡፡ በዚህ የወንጌል ክፍል ጌታችን በቤተ ሳይዳ ሕሙማንን እንደ ፈወሰ ተነግሮአል፡፡ ብዙ ሕሙማን ፈውስ ሽተው አንዲት የመጠመቂያ ሥፍራን ከበው ይኖሩ ነበር፡፡ በዚያች ሥፍራ ቀድሞ የወረደ እና የተጠመቀ አንድ በሽተኛ ብቻ ይፈወስ ነበር፡፡ ጌታችን በዚህ ሥፍራ ተገኝቶ በሽተኞችን ጐብኝቷል፡፡ በዚያም ልዩ ልዩ ደዌ ያለባቸው አምስት ዓይነት ሕሙማን እንደ ነበሩ ተገልጧል፤ እነዚህም፡- ሰውነታቸው የደረቀ፣ የሰለለና ያበጠ፤ እንደዚሁም ዕውራን እና ሐንካሳን ነበሩ፡፡ ከዚህ አምስት የተለያየ ዓይነት በሽታ ከተያዙ ሰዎች መካከል ደዌው የጸናበት፣ ለሠላሳ ስምንት ዓመታት በደዌ ዳኛ፣ ባልጋ ቍራኛ ተይዞ የኖረው፤ ከደዌው ጽናት የተነሣ ‹መጻጒዕ› ተብሎ የተጠራው በሽተኛ አንዱ ነበር፡፡ መጻጒዕ ስም አይደለም፡፡ ደዌ የጸናበት በሽተኛ ሕመምተኛ ማለት ነው እንጂ፡፡ ሰውየው ከበሽታው ጽናት የተነሣ ስሙ ጠፍቶ በበሽታው ሲጠራ የነበረ ነው፡፡ አምላካችን ይህን ሰው ‹‹አልጋህን ተሸክመህ ሒድ›› ብሎ ሠላሳ ስምንት ዘመን የተኛበትን አልጋ ተሸክሞ ወደ ቤቱ እንዲገባ ማድረጉ የሚነገርበት ወቅት በመኾኑ ሳምንቱ ‹መጻጒዕ› ተብሎ በተፈወሰው በሽተኛ ስም ተሰይሟል፡፡ (ሙሉ ታሪኩን በዮሐንስ ወንጌል ፭፥፩-፲፯ ይመልከቱ)፡፡ ዛሬም ቢኾን በሰዎች ላይ ልዩ ልዩ ደዌያት አሉ፤ የሥጋውን ደዌ ሐኪሞች ያውቁታል፡፡ ከዚህ የከፉ የነፍስ ደዌያት እጅግ ብዙዎች ናቸው፡፡ በኃጢአት ብዛት ልባቸው የደረቀና ያበጠ፤ ሰውነታቸው የሰለለ፤ ዓይነ ሕሊናቸው የታወረ፤ እግረ ልቡናቸው የተሰበረ ብዙዎች ሕሙማን አሁንም አሉ፡፡ ፈውስን ይሻሉ፤ ድኅነትን ይፈልጋሉ፡፡ እንደ መጻጕዕ ቦታቸውን ሳይለቁ እግዚአብሔርን በተስፋ ቢጠብቁት አንድ ቀን ይፈወሳሉ፡፡

ደብረ ዘይት

አምስተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ‹ደብረ ዘይት› ይባላል፡፡ ስያሜው የተወሰደውም ከማቴዎስ ወንጌል ፳፬፥፫ ካለው ትምህርት ነው፡፡ ደብረ ዘይት ከኢየሩሳሌም በስተምሥራቅ አቅጣጫ የሚገኝ በወይራ ዛፎች የተሸፈነ ትልቅ ተራራ ነው፡፡ ጌታችን ምሥጢራትን በተለያየ ቦታ ገልጧል፡፡ ምሥጢረ ጸሎትን በጌቴሴማኒ፤ ምሥጢረ መንግሥቱን በደብረ ታቦር፤ ምሥጢረ ቊርባንን በቤተ አልዓዛር፤ ምሥጢረ ትንሣኤ ሙታንን በቤተ ኢያኢሮስ፤ ምሥጢረ ምጽአቱን ደግሞ በደብረ ዘይት ገልጧል፡፡ ደብረ ዘይት ጌታችን ዳግም ለፍርድ መምጣቱንና ምሥጢረ ምጽአቱን ለደቀ መዛሙርቱ በሚገባ የገለጠበት ዕለት ነው፡፡ ደብረ ዘይትን ጌታችን በመዋዕለ ስብከቱ ለማደሪያነት ተጠቅሞበታል፡፡ ቀን ቀን በምኲራብ ያስተምራል፤ ሌሊት ሌሊት ደግሞ በደብረ ዘይት ያድራል፡፡ ይህንም ቅዱስ መጽሐፍ እንዲህ በማለት ይመሰክራል፤ ‹‹ዕለት ዕለት በመቅደስ ያስተምር ነበር፡፡ ሌሊት ግን ደብረ ዘይት ወደምትባል ተራራ ወጥቶ ያድር ነበር፡፡ ሕዝቡ ዅሉ ይሰሙት ዘንድ ማልደው በመቅደስ ወደ እርሱ ይመጡ ነበር›› (ሉቃ. ፳፩፥፴፯)፡፡ በዚህ ለማደሪያነት ባገለገለው ተራራ ምሥጢረ ምጽአቱን ስለ ገለጠበት አምስተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ደብረ ዘይት የሚል ስያሜ ተሰጥተታል፡፡ ደብረ ዘይት ጾሙ እኩል የሚኾንበት፤ አምላካችን በግርማ መንግሥቱ ለፍርድ በመጣ ጊዜ መልካም ለሠሩ ክብርን፣ ክፉ ለሠሩ ቅጣቱን የሚያስተላልፍ መኾኑ የሚነገርበት፤ ስለ ዓለም መጨረሻ እና ስለሚመጣው ሕይወት የምንማርበት የክርስቲያኖች ማስጠንቀቂያ ዕለት ነው፡፡

ገብር ኄር

ስድስተኛው ሳምንት ‹ገብር ኄር› የሚል ስያሜ አለው፡፡ ‹ገብር ኄር› ማለት ‹በጎ፣ ታማኝ አገልጋይ› ማለት ነው፡፡ ስያሜው ከማቴዎስ ወንጌል ፳፭፥፲፬ የተወሰደ ሲኾን፣ ታሪኩም እግዚአብሔር በሰጠው ጸጋ በታማኝነት ማገልገል የሚያስገኘውን ዋጋ ያስረዳል፡፡ አንድ ሰው አገልጋዮቹን ጠርቶ ወጥተው፣ ወርደው፣ ነግደው እንዲያተርፉ ለአንዱ አምስት፤ ለአንዱ ሁለት፤ ለአንዱ ደግሞ አንድ መክሊት ሰጣቸው፡፡ አምስት መክሊት የተቀበለው በተሰጠው መክሊት ነግዶ፣ ሌላ አምስት መክሊት አትርፎ፣ ዐሥር አድርጎ፣ ‹‹ጌታዬ አምስት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር፤ ወጥቼ ወርጄ አምስት አትርፌአለሁ›› ብሎ ለጌታው አቀረበ፡፡ ጌታውም ‹‹አንተ ጎበዝ እና ታማኝ ባሪያ! በጥቂቱ ታምነሃልና በብዙ እሾምሃለሁ፤ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ!›› አለው፡፡ ሁለት መክሊት የተቀበለውም ወጥቶ፣ ወርዶ፣ አትርፎ አራት አድርጎ አቀረበ፡፡ እርሱንም ጌታው ‹‹አንተ ታማኝ ባሪያ በጥቂቱ ታምነሃልና ወደ ጌታህ ደስታ ግባ!›› አለው፡፡ አንድ የተቀበለው ሰው ግን መክሊቱን ወስዶ ቀበራት፡፡ ጌታው በተቈጣጠረው ጊዜም የቀበራትን መክሊት አምጥቶ ‹‹አንተ ካልዘራህበት የምታጭድ፣ ካልበተንህበት የምትሰበስብ ጨካኝ እንደ ኾንኽ ዐውቃለሁ፡፡ ስለዚህ ፈራሁና የሰጠኸኝን መክሊት ቀበርኳት፤ እነሆ መክሊትህ!›› ብሎ ምንም ሳያተርፍ መክሊቱን ለጌታው መልሶ አስረከበ፡፡ ጌታውም ‹‹አንተ ክፉና ሐኬተኛ ባሪያ! ወርቄን በጊዜው አታስረክበኝም ነበር? ነግዶ ለሚያተርፍ እሰጠው ነበር፡፡ ይህን ክፉና ሐኬተኛ ባሪያ እጅ እግሩን አስራችሁ ጨለማና ጥርስ ማፋጨት ወዳለበት ሥፍራ ውሰዱት! መክሊቱን ቀሙና ለባለ ዐሥሩ ጨምሩለት!›› ብሎ አዘዘ፡፡

በዚህ ታሪክ እንደምናየው በተሰጠው መክሊት ያተረፈ ሰው (ክርስቲያን) ዋጋ አለው፡፡ በፈጣሪው ዘንድ መልካም፣ በጎ፣ ታማኝ ባሪያ ተብሎ ይሸለማል፡፡ ባያተርፍ ደግሞ ሐኬተኛ ባሪያ (አገልጋይ) ይባላል፤ ቅጣቱንም ይቀበላል፡፡ እንግዲህ እኛም ታማኝ አገልጋይ መኾን ይጠበቅብናል፡፡ ሳምንቱ ይህ መልእክት የሚተላለፍበት ወቅት ነው፡፡ በዚህ ዘመን በመክሊታቸው የሚያተርፉ እንዳሉ ዅሉ፣ መክሊታቸውን (ጸጋቸውን) ዝገት እስከሚያጠፋው ድረስ የሚቀብሩ ብዙዎች ናቸው፡፡ መክሊትን (ጸጋን) መቅበር ዋጋ የማያሰጥ መኾኑን ተገንዝበን በቻልነው መጠን ለማትረፍ መትጋት እና ታማኝ አገልጋይ መኾን እንደሚገባን ከገብር ኄር ታሪክ እንማራለን፡፡

ኒቆዲሞስ

ሰባተኛው ሳምንት ‹ኒቆዲሞስ› የሚል ስያሜ ያለው ሲኾን፣ የስያሜው መነሻም በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ ፫ የተመዘገበው ኒቆዲሞስ የተባለው የአይሁድ አለቃ ታሪክ ነው፡፡ ኒቆዲሞስ በሦስት መንገድ የአይሁድ አለቃ ነበር፤ በሥልጣን፣ በዕውቀትና በሀብት፡፡ ሰው ሥልጣን ቢኖረው ሀብትና ዕውቀት ላይኖረው ይችላል፡፡ ዕውቀት ቢኖረው ደግሞ ሀብትና ሥልጣን ላይኖረው ይችላል፡፡ ሀብት ቢኖረውም ዕውቀትና ሥልጣን ላይኖረው ይችላል፡፡ ኒቆዲሞስ ግን ሦስቱንም አንድ ላይ አስተባብሮ የያዘ የአይሁድ አለቃ ነበር፡፡ ኒቆዲሞስ ወንጌልን ለመማር ከአይሁድ ዅሉ ቀድሞ በሌሊት ወደ ጌታችን ይሔድ ነበር፡፡ ኒቆዲሞስ ፈሪሳውያን ማመን ባልቻሉበት በዚያን ዘመን ጆሮውን ለቃለ እግዚአብሔር፤ ልቡን ለእምነት የከፈተ ሰው ነው፡፡ ብዙ ሰዎችን እናውቃለን ማለት ከመልካም ነገር ሲከለክላቸው ኒቆዲሞስ ግን ዐዋቂ ሳለ ራሱን ዝቅ አድርጎ፣ እምነት በማጣት የነጠፈችውን የፈሪሳውያንን ኅብረት ጥሎ፣ ሐዋርያትን መስሎ ጌታውን አግኝቶታል፡፡ ጌታችን ዓለምን ለማዳን ቅድስት ነፍሱን ከቅዱስ ሥጋው በለየባት በዚያች አስጨናቂ ሰዓት፤ ሐዋርያት በተበተኑባት አይሁድ በሠለጠኑባት በዕለተ ዓርብ የጌታችንን ቅዱስ ሥጋውን በድርብ በፍታ ገንዞ የቀበረ፣ እሱን ያገኘ ያገኘኛል ሳይል በድፍረት ከእግረ መስቀሉ የተገኘ ሰው ነው – ኒቆዲሞስ፡፡ ስለዚህም ሰባተኛው ሳምንት በእርሱ ስም ተሰይሟል፡፡

ሆሣዕና

‹ሆሣዕና› ስምንተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ሲኾን፣ የሰሙነ ሕማማት መጀመሪያ ነው፡፡ ሆሣዕና ስያሜው በማቴዎስ ወንጌል ፳፩፥፱ ከሚገኘው ትምህርት የተወሰደ ሲኾን ትርጕሙም ‹መድኀኒት ወይም ‹አሁን አድን› ማለት ነው፡፡ ክብር ይግባውና አምላካችን በአህያ ጀርባ ላይ ተቀምጦ ‹‹ሆሣዕና በአርያም›› የሚሉ የአዕሩግ፣ የሕፃናት ምስጋና እየቀረበለት ወደ ኢየሩሳሌም ቤተ መቅደስ ጉዞ ያደረገበት፤ ትሕትናውን የገለጠበት፤ ይህን ዓለም ከማዕሠረ ኃጢአት መፍታቱን በምሳሌ ያስረዳበት ዕለት ነው፡፡ ‹‹ተጽዕኖ›› ተብሎ ከሚጠራው የዐቢይ ጾም መጨረሻ (ዕለተ ዓርብ) እና ከሰሙነ ሕማማት መግቢያ ጀምሮ ያለው ሳምንት ሆሣዕና ይባላል፡፡ የክርስቶስን ነገረ ሕማሙን፣ ስቅለቱን፣ ሞቱን፣ ትንሣኤውን ሆሣዕና ተብሎ ዓለምን ማዳኑን የሚናገሩ ቅዱሳት መጻሕፍት የሚነበቡበት፤ አምላካችን ለሰው ልጅ መዳን መከራ መቀበሉና የማዳን ሥራው በሰፊው የሚታወጅት፤ በሰሙነ ሕማማት ለሚያርፉ ምእመናን ጸሎተ ፍትሐት የሚደረግበት፤ ወንጌል በአራቱ ማዕዘን የሚሰበክበት ሳምንት ነው – ሆሣዕና፡፡ ከዚያው አያይዞም ሰሙነ ሕማማት ይቀጥላል፤ ወቅቱም የክርስቶስን ነገረ ሕማሙንና ዓለምን ያዳነበት ጥበቡን የምንሰማበት ሳምንት ነው፡፡ በሞቱ ሞታችንን አጥፍቶ መንግሥቱን እንድንወርስ የፈቀደልን ልዑል እግዚአብሔር ስሙ የተመሰገነ ይኹን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

‹‹ጾመ እግዚእነ አርአያሁ ከመ የሀበነ፤ አርአያነቱን ይሰጠን ዘንድ ጌታችን ጾመ፤›› (ቅዱስ ያሬድ)፡፡

በመምህር ምሥጢረ ሥላሴ ማናየ

መጋቢት ፲፩ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ጾም በብሉይ ኪዳንም በሐዲስ ኪዳንም በፈጣሪ መኖር ለሚያምኑ፣ የፈጣሪያቸውን ስም ጠርተው ለሚማጸኑ ዅሉ የተሰጠ አምላካዊ ትእዛዝ ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን ለሰዎች ከእግዚአብሔር ጋር መገናኛነት ያገለገሉ፣ በነቢያት የተጾሙ አጽዋማት እንዳሉ መጻሕፍት ይመሰክራሉ፡፡ ‹‹ሙሴም ወደ ተራራው ወጣ ዐርባ መዓልትና ዐርባ ሌሊት ቆየ፤›› (ዘጸ. ፳፬፥፲፰) ተብሎ እንደ ተጻፈው ሙሴ በተራራው የቆየው እየጾመ ነበር፡፡ ነቢያት በጾም ከፈጣሪያቸው ጋር ተገናኝተውበታል፡፡ ምንም እንኳን ድኅነተ ነፍስን ማግኘት ባይችሉም በመጾማቸው አባር፣ ቸነፈርን ከሕዝቡ አርቀዋል፡፡ በብሉይ ኪዳን ያሉ አጽዋማት በሙሉ በፍጡራን የተጾሙ ናቸው፡፡ የሐዲስ ኪዳን ጾም ግን የተጀመረው በጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ የብሉይ ኪዳን አጽዋማት ረድኤተ እግዚአብሔር የሚገኝባቸው፣ ለሐዲስ ኪዳን አጽዋማት መነሻና ምሳሌዎች ናቸው፡፡

ቅዱስ ያሬድ ከላይ በርእሱ በተጠቀሰው ኃይለ ቃል እንደ ገለጸው የጌታችን ጾም የሐዲስ ኪዳን አጽዋማት መጀመሪያ ነው፡፡ ይህ ጾም የአጽዋማት ዅሉ በኵር ነው፡፡ በኃጢአት ብዛትና በመርገም በጠወለገ ሰውነት የተጾሙ አጽዋማትን ጌታችን አድሷቸዋል፤ ቀድሷቸዋልም፡፡ ውኃ ከላይ ደጋውን፣ ከታች ቆላውን እንዲያለመልም፣ የጌታችንም ጾም ከላይ ከመጀመሪያ የነበረ የአበውን ጾም ቀድሷል፤ ጉድለቱንም ሞልቷል፡፡ ጌታችን ጾሞ ከእርሱ በኋላ የተነሡ ሐዋርያትን፣ ጻድቃንን፣ ሰማዕታትን፣ ደናግልን፣ መነኮሳትን በአጭሩ የምእመናን ጾም ቀድሷል፡፡ በአጠቃላይ የጌታችን ጾም እንደ በር ነው፡፡ በር ሲከፈት ከውጭ ያለውን እና ከውስጥ ያለውን ያገናኛል፡፡ የጌታችን ጾምም ከፊት የነበሩትን የነቢያትን አጽዋማት ኋላ ከተነሡ ከሐዋርያት አጽዋማት ጋር ያገናኘ፤ በመርገም ውስጥ የነበሩትንና ከመርገም የተዋጁትን ያስተባበረ ጾም ነው፡፡

‹‹ጌታችን የጾመው ለምን ነው?›› የሚለውን ትልቅ ጥያቄ ‹‹አርአያነቱን ይሰጠን ዘንድ ጾመ›› በማለት ቅዱስ ያሬድ መልሶልናል፡፡ ጌታችን የጾመው እንደ ፍጡራን ክብር ለመቀበል ኃጢአት ኖሮበት ስርየት ለማግኘት አይደለም፡፡ አርአያነቱን አይተን፣ ፍለጋውን ተከትለን ልንጠቀምበት ጾምን ቀድሶ ሰጠን፡፡ ጾም ዲያብሎስን ድል የምንነሣበት ጋሻ፣ ከኃጢአት የምንሰወርበት ዋሻ የመንግሥተ ሰማያት መውረሻ፣ መኾኑን አርአያ ኾኖ ሊያሳየን ጌታችን ጾመ፡፡ የጾምንም ጥቅም በግብር (በተግባር) አስተማረን፤ አስረዳን፡፡ ይህ የጌታችን ጾም – ‹ዐቢይ (ታላቅ) ጾም፣ ሁዳዴ፣ ዐርባ ጾም፣ የጌታ ጾም› እየተባለ ይጠራል፡፡ ዐቢይ ጾም ማለት ከግሱ እንደምንረዳው እጅግ ትልቅ ጾም ማለት ነው፡፡ በእርግጥ የጾም ትንሽ የለውም፤ አንድም ቀን ይሁን ሳምንት ጾም ትልቅ ነው፡፡ የጌታችን ጾም የታላቆች ታላቅ፣ የነገሥታት ንጉሥ፣ የጌቶች ዅሉ ጌታ፣ የፍጥረታት ዅሉ ፈጣሪ ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ጾመው ነው፤ ስምንት ሳምንታን፣ ኀምሳ አምስት ቀናትን በውስጡ የያዘ፣ በቊጥርም ከአጽዋማት ዅሉ እጅግ ከፍ ያለና የሐዲስ ኪዳን አጽዋማት ዅሉ በኵር ስለ ኾነ ዐቢይ (ታላቅ) ጾም ይባላል፡፡

ሁዳድ (የመንግሥት እርሻ)፡- በአንድ መንግሥት የሚተዳደሩ ሕዝቦች በሙሉ በግዳጅ ወጥተው የሚያርሱበት፣ የሚዘሩበት፣ የሚያጭዱበት መሬት እንደ ኾነ ዅሉ ይህም ጾም የጌታችን የመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን የመንግሥቱን የምስራች በምትነግር ወንጌል ያመኑ ምእመናን በአዋጅ በአንድነት የሚጾሙት ጾም በመሆኑ ‹ሁዳድ› ተብሎ ይጠራል፡፡ ‹ዐርባ ጾም› የተባለበት ምክንያትም ጌታችን የጾመው ዐርባ መዓልትና ዐርባ ሌሊት ስለ ኾነ ነው፡፡ ‹‹ዐርባ መዓልትና ዐርባ ሌሊት ጾመ›› እንዲል (ማቴ. ፬፥፪)፡፡ ጾሙ ስምንት ሳምንታትን ኀምሳ አምስት ቀናትን ያካተተ ነው ብለናል፡፡ ጌታችን የጾመው ዐርባ ቀን ነው፡፡ ለምን ኀምሳ አምስት ቀናት እንጾማለን? የሚሉ ጥያቄዎች በውስጣችን ሊመላለሱ ይችላሉ፡፡

ጌታችን በጾመው ዐርባ ቀን ላይ ቅዱሳን ሐዋርያት ከመጀመሪያው አንድ ሳምንት ከመጨረሻው አንድ ሳምንት ጨምረውበታል፡፡ በዚህ ምክንያት ጾሙ ከስድስት ወደ ስምንት ሳምንታት፣ ከዐርባ ወደ ኀምሳ አምስት ቀናት ከፍ ሊል ችሏል፡፡ ለምን ብለን ጥያቄ ማንሣት የለብንም፡፡ ምክንያቱን ቀኑን የጨመሩት ከጌታችን ጋር የዋሉ በቃልም፣ በተግባርም ከጌታችን የተማሩት፣ የምሥጢር ደቀ መዛሙርት፣ የሕግ ምንጮች፣ እኛ ወደ ክርስቶስ የምናደርገው ጉዞ መሪዎች ቅዱሳን ሐዋርያት ናቸውና፡፡ እኛ የክርስትና ተቀባዮች እንጂ ጀማሪዎች ወይም መሥራቾች አይደለንም፡፡ በቅዱሳን ሐዋርያት መሠረትነት ላይ ተመሠረትን እንጂ፡፡ ‹‹እናንተስ በነቢያትና በሐዋርያት መሠረትነት ላይ ተመሥርታችኋል›› እንዳለ ቅዱስ ጳውሎስ (ኤፌ. ፪፥፳)፡፡ እናም ሕጋቸውንና ሥርዓታቸውን አምነን ከመቀበል ውጭ መቃወም አይቻለንም፡፡ የብሎኬት ድርድር መሠረት አያስፈልገኝም ሊል አይችልም፡፡ መሠረቱ ከተናደ ድርድሩ የት ሊቆም ይችላል? እኛም የሐዋርያትን ትእዛዝ ካልተቀበልን የማንን ትእዛዝ እንቀበላለን?

ቅዱሳን ሐዋርያት ከመጀመሪያው የጨመሩት የጌታችን ጾም መግቢያ መቀበያ ንጉሥ ሲመጣ በሠራዊት እንዲታጀብ፣ በብዙ ሕዝብ እንዲከበብ፣ ሕዝቡ ከፊት ከኋላ ከበውና አጅበው በክብር እንደሚቀበሉትና እንደሚሸኙት ዅሉ የንጉሣችን የኢየሱስ ክርስቶስ ጾም ሲመጣም እንደ ሕዝብ፣ እንደ ሠራዊት የሚያጅቡ፣ የሚከቡ፣ የሚያከብሩ ሳምንታትንና ዕለታትን ማለትም ከመጀመሪያው ዘወረደን፤ ከመጨረሻው ደግሞ ሕማማትን ጨምረዋል፡፡ ደግሞም መልካም ምግባርንም ኾነ የጾምን ቀን መቀነስ እንጂ መጨመር አያስቀጣም፡፡ በክርስትና ሕይወት የተቀበሉትን መክሊት መቅበር እንጂ አትርፎ ማቅረብ ያስከብራል፤ ገብር ኄር (ታማኝ አገልጋይ) ያሰኛል፤ ያሾማል፤ ያሸልማል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡