ክርስቲያናዊ ኑሮ በዘመነ አስተምሕሮ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ታኅሣሥ ፲ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

በቤተ ክርስቲያናችን የወቅት አከፋፈል ሥርዓት ከኅዳር ፮ እስከ ታኅሣሥ ፯ ቀን የሚገኘው ወቅት ‹ዘመነ አስተምህሮ› ይባላል፡፡ ቀጣዩ ወቅት (ዘመነ ስብከት) ዕለተ ሰንበትን ጠብቆ የሚገባ በመኾኑ ይህ ወቅት አንዳድ ጊዜ እስከ ታኅሣሥ ፲፫ ቀን የሚዘገይበት ጊዜም አለ፡፡ ‹ዘመነ አስተምህሮ› የሚለው ሐረግ ትርጕሙም በሃሌታው ‹ሀ› (‹አስተምህሮ› ተብሎ) ሲጻፍ የቃለ እግዚአብሔር ማስተማሪያ ማለትም የትምህርተ ወንጌል ዘመን ማለት ነው፡፡ ሥርወ ቃሉም ‹‹መሀረ/አምሀረ – አስተማረ፤ ለመምህር ሰጠ፤  መራ፤ አሳየ፤ መከረ፤ አለመደ›› ወይም ‹‹ተምህረ – ተማረ፤ ለመደ›› የሚለው የግእዝ ግስ ነው (ኪዳነ ወልድ ክፍሌ፣ ገጽ ፭፻፸፱)፡፡ 

ይኸውም የእግዚአብሔርን ቸርነት፣ ርኅራኄ፣ ትዕግሥትና የማዳን ሥራውን የሚመለከት ትምህርት በስፋት የሚቀርበበት ጊዜ ነው፡፡ ቃሉ በሐመሩ ‹‹ሐ›› (‹አስተምሕሮ› ተብሎ) ሲጻፍ ደግሞ የምሕረት፣ የይቅርታ ዘመን ማለት ነው፡፡ ሥርወ ቃሉም ‹‹መሐረይቅር አለ፤ ዕዳ በደልን ተወ›› ወይም ‹‹አምሐረ – አስማረ፤ ይቅር አሰኘ፤ አራራ፤ አሳዘነ›› የሚለው የግእዝ ግስ ነው (ኪዳነ ወልድ ክፍሌ፣ ገጽ ፭፻፹፬)፡፡

ጠቅለል አድርገን ስንመለከተው ዘመነ አስተምሕሮ ስለ እግዚአብሔር ቸርነትና ርኅራኄ፤ እርሱ በደላችንን ዅሉ ይቅር እንደሚለን እኛ ምእመናንም እርስበርስ ይቅር መባባል እንደሚገባን ትምህርት የሚሰጥበት ጊዜ ነው፡፡

በቅዱስ ያሬድ የዜማ መጻሕፍት እንደ ተቀመጠው በዘመነ አስተምሕሮ ውስጥ የሚገኙ ሰንበታት (እሑዶች) አስተምሕሮ፣ ቅድስት፣ ምኵራብ፣ መጻጉዕ እና ደብረ ዘይት ተብለው ይጠራሉ፡፡ ከመጀመሪያው ሳምንት (ከአስተምሕሮ) በቀር የአራቱ እሑዶቹ ስያሜ ከዐቢይ ጾም ሰንበታት ጋር አንድ ዓይነት ነው፡፡ የሰንበታቱ ስያሜ ከዐቢይ ጾም ሰንበታት ጋር ተመሳሳይ ይኹን እንጂ በእነዚህ ሳምንታት ሌሊት የሚዘመሩ መዝሙራት፣ በቅዳሴ ጊዜ የሚነበቡ ምንባባትና የሚቀርቡ ትምህርቶች ግን በምሥጢር ይለያያሉ፡፡

ትምህርቶቹ ይለያያሉ ስንልም በዚህ ወቅት የሚነገረው ምሥጢርና ይዘት በወቅቱ ላይ የሚያተኵር መኾኑን ለመግለጽ ነው እንጂ በየትኛውም ጊዜ በቤተ ክርስቲያናችን የሚቀርበው ትምህርት አንዱ የእግዚአብሔር ቃል ብቻ ነው። ሳምንታቱን በዚህ መልክ የከፋፈለውም ሊቁ ቅዱስ ያሬድ ነው፡፡ ይህንንም ከመጽሐፈ ድጓው መመልከት ይቻላል (ድጓ ዘአስተምህሮ)፡፡

ከዚህ ቀጥለን በእያንዳንዱ የዘመነ አስተምህሮ (አስተምሕሮ) ሳምንት የሚቀርበውን ትምህርት በቅደም ተከተል በአጭሩ እንመለከታለን፤

፩. አስተምሕሮ

የመጀመሪያው የዘመነ አስተምሕሮ ሳምንት አስተምሕሮ ይባላል፤ ይህም ከኅዳር ፮–፲፪ ያሉትን ሰባት ቀናት ያካትታል፡፡ በዕለቱ (እሑድ) የሚቀርበው የቅዱስ ያሬድ መዝሙር ‹‹ኢተዘኪሮ አበሳ ዚአነ ኢኀደገነ ፍጹመ ንማስን …. ኀጢአታችንን አላሰበብንም፤ እንጠፋ ዘንድም ፈጽሞ አልተወንም ….›› የሚለው ሲኾን፣ በተጨማሪም ‹‹ፈጽም ለነ ሠናይተከ እንተ እምኀቤነ …. በአንተ ዘንድ ያለችውን በጎነት ፈጽምልን ….›› የሚለውም እንደ አማራጭ ሊዘመር ይችላል፡፡ ምስባኩ ‹‹ኢትዝክር ለነ አበሳነ ዘትካት ፍጡነ ይርከበነ ሣህልከ እግዚኦ እስመ ተመንደብነ ፈድፋደ፤ የቀደመውን በደላችንን አታስብብን፡፡ አቤቱ ምሕረትህ ፈጥኖ ያግኘን፡፡ እጅግ ተቸግረናልና፤›› የሚለው የዳዊት መዝሙር ነው (መዝ. ፸፰፥፰)፡፡

ወንጌሉ ማቴዎስ ፮፥፭-፲፮ ሲኾን፣ ይኸውም ፊትን በማጠውለግና ጸሎተኛ በመምሰል ሳይኾን በፍጹም ፍቅርና ትሕትና መጾም መጸለይ እንደሚገባን የሚያስተምረው የወንጌል ክፍል ነው፡፡ እንደዚሁም ከእግዚአብሔር ዘንድ ይቅርታን ለማግኘት በመጀመሪያ እርስበርሳችን ይቅር መባባል ማለትም የበደሉንን ይቅር ማለት እንዳለብን ይህ የወንጌል ክፍል ያስረዳናል፡፡ ቅዳሴውም ቅዳሴ እግዚእ (የጌታችን ቅዳሴ) ምሥጢረ ሥላሴን፣ ምሥጢረ ሥጋዌንና ነገረ ድኅነትን ከምሥጢረ ቍርባን ጋር በማስማማት የተዘጋጀውና ብዙ ምሥጢራትን ያካተተው ቅዳሴ ነው፡፡

በዚህ ሳምንት (በአስተምሕሮ) እግዚአብሔር አምላካችን ከአምስት ሺሕ አምስት መቶ ዓመት የመርገምና የጨለማ ዘመን ዓለምን ማውጣቱ፤ ቸርነቱ፣ ርኅራኄውና ትዕግሥቱ፤ ምእመናንን ከሞተ ሥጋ ከሞተ ነፍስ ማዳኑ በሰፊው ይመሠጠርበታል፡፡ በየጊዜው እንደምንማረው እግዚአብሔር አምላካችን ከሰማየ ሰማያት ወርዶ፣ ከቅድስት ደንግል ማርያም ተወልዶ በአዳም በደል (የውርስ ኀጢአት) ምክንያት ከመቀጣት ማለትም ከሞተ ነፍስ (ከቁራኝነት) አድኖናል፡፡ ድነናል ስንልም ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በከፈለው መሥዋዕትነት በቀደመው የአዳም በደል አንጠየቅም ማለታችን ነው፡፡

ይኹን እንጂ በየራሳችን በደል እንደምንጠየቅ መዘንጋት የለብንም፡፡ ስለዚህም ‹‹በጸጋው ድነናል›› እያሉ ከጽድቅ ሥራ ተለይተው በዘፈቀደ ምድራዊ ኑሮ ማለፍ ከሚፈልጉ አንዳንድ ሰዎች የተሳሳተ ትምህርት መራቅ ይጠበቅብናል፡፡ ከዚሁ ዂሉ ጋርም ‹‹ድነናል›› ብለን ብቻ መቀመጥ ሳይኾን የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ እንችል ዘንድ በየጊዜው ከሠራነው ኀጢአት በንስሐ መመለስ እንደሚገባንም መረዳት ይኖርብናል፡፡ ይኸውም (ምሥጢረ ንስሐ) እግዚአብሔር አምላካችን ለእኛ ለምእመናን የሰጠን ልዩ ጸጋ ነው፡፡

ይህን ያህል ጸጋ ከተሰጠን ለመኾኑ በምን ዓይነት ሕይወት እየኖርን ነው? በመንፈሳዊ ወይስ በዓለማዊ? በፈሪሃ እግዚአብሔር ወይስ በአምልኮ ባዕድ? በጽድቅ ወይስ በኀጢአት ሥራ? ጥያቄውን ለየራሳችን እንመልሰው፡፡ በፈቃዱ ከሞት ወደ ሕይወት የመለሰንን አምላክ በክፉ ግብራችን እንዳናሳዝነው ልንጠነቀቅ ያስፈልጋል፡፡ በመልካምታችን ከዂሉም በፊት የምንጠቀመው እኛው ራሳችን ነንና፡፡

ስለዚህ በዚህ ወቅት እግዚአብሔር ያደረገልንን ዘለዓለማዊ ውለታ በማሰብ ይቅርታውን፣ ቸርነቱን ከማድነቅና እርሱን ከማመስገን ባሻገር በጽደቅ ሥራ ልንበረታ ይገባናል፡፡ ጊዜው የአስተምሕሮ ማለትም የምሕረት፣ ይቅርታ፣ የስርየተ ኀጢአት እንደዚሁም የምስጋና ጊዜ ነውና፡፡

፪. ቅድስት

ከኅዳር ፲፫–፲፱ ያሉትን ሰባት ቀናት የሚያካትተው የዘመነ አስተምሕሮ ሁለተኛው ሳምንት ቅድስት ይባላል፤ ቅድስት የተባለበት ምክንያትም ዕለተ ሰንበትን ለቀደሰ፣ ለመረጠ፣ ላከበረ ለልዑል እግዚአብሔር ክብር ምስጋና ማቅረብ እንደሚገባ የሚነግርበት ሳምንት በመኾኑ ነው፡፡ በዚህ ዕለት (እሑድ) ‹‹ሎቱ ስብሐት ወሎቱ አኰቴት ለዘቀደሳ ለሰንበት …. ሰንበትን ላከበራት ለእርሱ ክብር ምስጋና ይኹን (ምስጋና ይድረሰው፤ ምስጋና ይገባዋል) ….›› የሚለው የቅዱስ ያሬድ መዝሙር ይቀርባል፡፡ በቅዳሴ ጊዜም ‹‹ኵሎ ዘፈቀደ ገብረ እግዚአብሔር በሰማይኒ ወበምድርኒ በባሕርኒ ወበኵሉ ቀላያት፤ በሰማይና በምድር፣ በባሕርና በጥልቆችም ዅሉ እግዚአብሔር የወደደውን ዅሉ አደረገ፤›› የሚለው ምስባክ ይሰበካል (መዝ. ፻፴፬፥፮)፡፡

የዕለቱ ወንጌል ዮሐንስ ፭፥፲፮-፳፰ ሲኾን፣ ይኸውም ስለ ሰንበት ክብር፣ እግዚአብሔር የሰንበት ጌታ ስለመኾኑና ሰንበትን ለሰው ልጆች ዕረፍት ስለ መፍጠሩ ያስረዳል፡፡ በዚህ ሳምንት ሰንበትን ስለ ቀደሰ እግዚአብሔር ቅድስና እና ሰንበት ቅድስት ስለመኾኗ ሰፊ ትምህርት ይቀርባል፡፡ በዕለቱ የሚቀደሰው ቅዳሴ አትናቴዎስም ነገረ ድኅነትን ከምሥጢረ ሥጋዌና ምሥጢረ ቍርባን ጋር በማስማማት የሚያትትና ክብረ ሰንበትን የሚያስረዳ ቅዳሴ ነው፡፡

ቅዱስ ያሬድ ‹‹ሰንበት ተዐቢ እምኵሉ ዕለት ወሰብእ ይከብር እምኵሉ ፍጥረት፤ ከዕለታት ሰንበት ትበልጣለች፤ ከምድራውያን ፍጥረታትም የሰው ልጅ ይከብራል›› በማለት እንደ ዘመረው ዕለተ ሰንበት ከሳምንቱ ዕለታት ዂሉ ትበልጣለች፡፡ የሰው ልጅም ከምድራውያን ፍጥረታት የከበረ ነው፡፡ ሰንበት ስንል ሁለቱን ዕለታት (ቀዳሚት ሰንበት እና እሑድ ሰንበትን) ማለታችን ነው፡፡ የመጀመሪያዋ ሰንበት እግዚአብሔር ከሥራው ዂሉ ስላረፈባት፤ ሁለተኛዋ (እሑድ) ሰንበት ደግሞ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ተፀነሰባት፣ ከሙታን ተለይቶ ስለ ተነሣባት ከዕለታት ዂሉ ይበልጣሉ፡፡ ስለዚህም ከሌሎች ዕለታት አስበልጠን እናከብራቸዋለን፡፡

የሰው ልጆችም በእግዚአብሔር መልክና ምሳሌ እንደ መፈጠራችን ከፍጥረታት ዂሉ እንደምንከብር ቅዱሳት መጻሕፍት ይነግሩናል፡፡ ኾኖም ብዙዎቻችን እግዚአብሔር የሰጠንን ክብር በራሳችን ኀጢአት ዝቅ አድርገነዋል፡፡ ማለትም በእግዚአብሔር አምሳል ከተፈጠረ፣ ለእግዚአብሔር ማደሪያነት ከተመረጠ ክቡር ሰው በማይጠበቅ ክፉ ግብር ወድቀናል፡፡ በዝሙት፣ እርስበርስ በመከፋፈል፣ በመገዳደል፣ በመተማማትና በሐሰት በመካከሰስ በጥቅሉ ለሰይጣናዊ ግብር በፈቃዳችን በመገዛት ራሳችንንና ሌሎችን የምንበድል፣ እግዚአብሔርንም የምናሳዝን ሰዎች ጥቂቶች አይደለንም፡፡ እግዚአብሔር ይቅር ብሎ ወደ ክርስቲያናዊ ሕይወትና ወደ መንፈሳዊ ሰብእና ይመልሰን እንጂ፡፡

ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት፣ ይህን ዂሉ የሰው ልጅ በደል ሲያመላክት ‹‹ሰብእሰ እንዘ ክቡር ውእቱ ኢያእመረ ወኮነ ከመ እንስሳ ዘአልቦ ልብ ወተመሰሎሙ፤ ሰው ግን ክቡር ኖ ሳለ አያውቅም፡፡ እንደሚጠፉ እንስሶች መሰለ፤›› በማለት ይናገራል (መዝ. ፵፰፥፲፪)፡፡ የቤተ ክርስቲያናችን ሊቃውንት በትርጓሜአቸው ‹‹ዳዊት አክብሮ አጓዶ ተናገረ፡፡ ዕዝራ ግን ‹እንስሳት ይኄይሱነ፤ እነስሳት ይሻሉናል› ብሎታል›› በማለት ይህንን ኃይለ ቃል ያመሠጥሩታል።

ምሳሌውን ሲያብራሩም ‹‹እንስሳ ከገደል አፋፍ ኖ ሲመገብ ከገደሉ ሥር ለምለም ሣር፣ ጥሩ ው ቢያይ የረገጠው መሬት ከአልከዳው (ከአልተናደበት) በስተቀር ወርጄ ልመገብ፣ ልጠጣ አይልም፡፡ ሰው ግን ጽድቅ እንዲጠቅም ኀጢአት እንዲጎዳ እያወቀ ጨለማን ተገን አድርጎ ሊሠርቅ፣ ሊቀማ፣ የጎልማሳ ሚስት ሊያስት ይሔዳል›› ሲሉ ያብራሩታል (ትርጓሜ መዝሙረ ዳዊት)፡፡

በዚህ ዓይነት ኀጢአት ራሳችንን ያስገዛን ዂሉ፣ ከዚህ ክፉ ግብራን በመለየት በንስሐ ወደ እግዚአብሔር መመለስ ከፍጥረታት ከከበርን ከሰው ልጀች ይልቁንም ከክርስቲያኖች ይጠበቃል፡፡ ስለዚህም አሁኑኑ ወደ ይቅር ባዩ አምላካችን ቀርበን ይቅርታን፣ ስርየትን እንለምን፡፡ ጊዜው ዘመነ አስተምሕሮ (የይቅርታ ዘመን) ነውና፡፡

፫. ምኵራብ

ሦስተኛው የዘመነ አስተምሕሮ ሳምንት ምኵራብ የሚባል ሲኾን ይህም ከኅዳር ፳–፳፮ ያሉትን ሰባት ቀናት የሚያካትት ሳምንት ነው፡፡ በዚህ ሳምንት ጌታችን፣ አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምኵራበ አይሁድ ሕዝቡን እየሰበሰበ ማስተማሩ፤ ባሕርና ነፋሳትን መገሠፁ፤ አጋንንትን ከሰዎች ማውጣቱ ይነገራል፡፡

በዕለቱ (እሑድ) የሚቀርበው መዝሙር፡- ‹‹አምላክ ፍጹም በህላዌሁ ዘሀሎ እምቅድመ ይትፈጠር ዓለም …. ዓለም ከመፈጠሩ አስቀድሞ የነበረው አምላክ (እግዚአብሔር) በህልውናው (አነዋወሩ) ፍጹም ነው ….››  የሚለው ሲኾን፣ ምስባኩም፡- ‹‹ቅረቡ ኀቤሁ ወያበርህ ለክሙ ወኢይትኀፈር ገጽክሙ ዝንቱ ነዳይ ጸርሐ ወእግዚአብሔር ሰምዖ፤ ወደ እርሱ ቅረቡ፤ ያበራላችሁማል፡፡ ፊታችሁም አያፍርም፡፡ ይህ ችግረኛ ጮኸ፤ እግዚአብሔርም ሰማው፤›› የሚል ነው (መዝ. ፴፫፥፭-፮)፡፡ ወንጌሉም ከማቴዎስ ፰፥፳፫ እስከ መጨረሻው ድረስ ነው፡፡ ቅዳሴውም ቅዳሴ እግዚእ ነው፡፡

የዕለቱ ወንጌል ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመርከብ ውስጥ ሳለ መርከቢቱ እስክትናወጥ ድረስ ታላቅ ማዕበል መነሣቱን፤ ቅዱሳን ሐዋርያት ‹‹ጌታ ሆይ እንዳንጠፋ አድነን?›› እያሉ በመተማጸኑት ጊዜ ጌታችን ነፋሱንና ባሕሩን በመገሠፅ ጸጥታን፣ ሰላምን፣ መረጋጋትን ማስፈኑን የሚናገረው ክፍል ነው፡፡

በባሕሩ ዓለም ውስጥ የምትገኘው ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ሰዎች በፈቃደ ሥጋቸው ተሸንፈው ባመጡት ጥላቻ፣ ኑፋቄ፣ ክህደት፣ ፍቅረ ንዋይ፣ በአጠቃላይ በልዩ ልዩ የኀጢአት ማዕበልና ሞገድ እየተናወጠች ናት፡፡ ይህን ማዕበልና ሞገድ ጸጥ በማድረግ ፍቅርን፣ አንድነትን፣ ሰላምንና ጽድቅን ማስፈን የሚቻለውን መድኀኒታችን ክርስቶስን እንደ ቅዱሳን ሐዋርያት በአንድነት ኾነን ‹‹ጌታ ሆይ እንዳንጠፋ አድነን?›› እያልን እንማጸነው፡፡

የሰላሙ ዳኛ፣ የሰላሙ መሪ፣ የሰላሙ ጌታ፣ የሰላሙ ንጉሥ፣ የሰላሙ ባለቤት እርሱ ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰላምን፣ መረጋጋትን፣ ፍቅርን፣ አንድነትን ካወጀ በቤተ ክርስቲያናችን ፍቅር፣ አንድነት ሰላም ይሰፍናልና፡፡

፬. መጻጕዕ

ከኅዳር ፳፯ እስከ ታኅሣሥ ፫ ያሉ ሰባት ቀናትን የሚያጠቃልለው አራተኛው የዘመነ አስተምሕሮ ሳምንት መጻጕዕ ይባላል፡፡ የቃሉ ፍቺ ‹በደዌ ዳኛ፣ በአልጋ ቍራኛ የተያዘ በሽተኛ ማለት ነው፡፡ ዕለቱ መጻጕዕ ተብሎ መሰየሙም ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዕውር ኾኖ የተወለደውን ጐበዝ ዓይን ያበራበትን ዕለት ለማስታወስ ነው፡፡

የዕለቱ (እሑድ) መዝሙር ‹‹ይቤሉ እስራኤል ኢርኢነ ወኢሰማዕነ ዘዕውሩ ተወልደ ወተከሥተ አዕይንቲሁ በሰንበት …. ዕውር ኾኖ ተወልዶ ዓይኖቹ በሰንበት የበሩለትን ሰው እስራኤልአላየንም፤ አልሰማንምአሉ ….›› የሚለው የእስራኤላውያንን በክርስቶስ ተአምር አለማመን የሚገልጸው የቅዱስ ያሬድ ድርሰት ነው፡፡

ምስባኩም ‹‹ደቂቀ ዕጓለ እመሕያው እስከ ማእዜኑ ታከብዱ ልበክሙ ለምንት ታፈቅሩ ከንቶ ወተሐሱ ሐሰተ አእምሩ ከመ ተሰብሐ እግዚአብሔር በጻድቁ፤ እናንት የሰው ልጆች፣ እስከ መቼ ድረስ ልባችሁን ታከብዳላችሁ? ከንቱ ነገርን ለምን ትወዳላችሁ? ሐሰትንም ለምን ትሻላችሁ? እግዚአብሔር በጻድቁ እንደ ተገለጠ ዕወቁ፤›› የሚለው እግዚአብሔር ለጻድቃኑ በሚያደርገው ድንቅ ሥራ ማመን እንደሚገባ የሚያስረዳው የዳዊት መዝሙር ነው (መዝ. ፬፥፪-፫)፡፡

ወንጌሉ ደግሞ ዕውር ኾኖ የተወለደውንና በጌታችን አምላካዊ ኃይል የተፈወሰውን ጐልማሳ ታሪክ የሚተርከው ዮሐ. ፱፥፩ እስከ መጨረሻው ያለው ኃይለ ቃል ሲኾን፣ የዕለቱ ቅዳሴም ቅዳሴ እግዚእ ነው፡፡ በዚህ ሳምንት መድኀኒታችን የዕውሩን ዓይን ከማብራቱ ባሻገር ሕሙማነ ሥጋን በተአምራቱ፤ ሕሙማነ ነፍስን በትምህርቱ ስለ ማዳኑ የሚያወሳ ቃለ እግዚአብሔር ይቀርባል፡፡

ትምህርቱን ከእኛ ሕይወት ጋር አያይዘን ስንመለከተው፣ ብዙዎቻችን ዓይነ ሕሊናችን የጽደቅ ሥራ ብርሃንን ከማየት በመሰወሩ የተነሣ በልዩ ልዩ ደዌ ተይዘናል፡፡ በሐሜት፣ በኑፋቄ፣ በጥላቻ፣ በዐመፅ፣ በስርቆት፣ በውሸት፣ በዝሙት፣ ወዘተ. በመሳሰሉት ደዌያት የተለከፍን ጥቂቶች አይደለንም፡፡ ለዚህም በልዩ ልዩ የዓለም ክፍሎች የምንሰማውና የምናየው በቂ ማስረጃ ነው፡፡

ሰው በሰው ላይ በጠላትነት ሲነሣሣና ወንድሙን፣ እኅቱን በአሰቃቂ ኹኔታ ሲገድል፤ ተመሳሳይ ፆታዎች በሰይጣናዊ ፈቃድ ተሸንፈው ‹ጋብቻ› ሲመሠርቱ፤ አንዳንዶቹ ከሕግ ባሎቻቸውና ሚስቶቻቸው ውጪ ሲዘሙቱ፤ ከዚህ በባሰ ደግሞ እግዚአብሔር ምእመናንን እንዲመሩ የሾማቸው ካህናት ሳይቀሩ ክብረ ክህነትን በሚያስነቅፍ የስርቆትና ሌላም ወንጀል ተሰማርተው የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ገንዘብ ሲመዘብሩ እየሰማን ነው፡፡

ከዚህ የሚበልጥ ደዌ ምን አለ? ከደዌ ሥጋ በጠበልና በሕክምና መፈወስ ይቻላል፡፡ በሽታው ባይድንም እንኳን ሕመሙን ለመቋቋም የሚያስችል መድኀኒት አይጠፋም፡፡ የኀጢአት ደዌ ግን መድኀኒቱ ንስሐ ብቻ ነው፡፡ ስለኾነም ከላይ በተጠቀሱትና በመሳሰሉት ደዌያት የምንሰቃይ ወገኖች ዂሉ ፈውሱ ዘለዓለማዊ ወደ ኾነው ወደ ወደ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቀርበን እንፈወስ፡፡ እርሱ የነፍስ የሥጋ መደኀኒት ነውና፡፡

፭. ደብረ ዘይት

አምስተኛውና የመጨረሻው የዘመነ አስተምሕሮ ሳምንት ‹ደብረ ዘይት በመባል የሚታወቅ ሲኾን የሚያጠቃልለውም ከታኅሣሥ ፬ – ፮ ያሉ ቀናትን ነው፡፡ በዕለቱ (እሑድ) ‹‹ሠርዐ ሰንበተ ለሰብእ ዕረፍተ ለእለ በሰማይ ወለእለ በምድር እግዚአብሔር በሰማይም በምድርም ለሚኖሩ ፍጡራን ሰንበትን ለዕረፍት ሠራ (ፈጠረ) ….›› የሚለው የቅዱስ ያሬድ መዝሙር ይዘመራል፡፡

‹‹ለነዳያኒሃኒ አጸግቦሙ እክለ ወለካህናቲሃኒ አለብሶሙ ሕይወተ ወጻድቃኒሃኒ ትፍሥሕተ ይትፌሥሑ፤ ባልቴቶቿን እጅግ እባርካቸዋለሁ፤ ድሆቿንም እኽልን አጠግባቸዋለሁ፡፡ ካህናቷንም ደኅንነትን አለብሳቸዋለሁ፡፡ ጻድቃኖቿም እጅግ ደስ ይላቸዋል፤›› የሚለው የዳዊት መዝሙር ደግሞ የዕለቱ ምስባክ ነው (መዝ. ፻፴፩፥፲፭-፲፮)፡፡

በዕለቱ የሚነበበው የወንጌል ክፍልም ሉቃስ ፲፪፥፴፪-፵፩ ሲኾን፣ ቅዳሴው ደግሞ ቅዳሴ አትናቴዎስ ነው፡፡ በዚህ ሳምንት ሰንበት የዕረፍት ዕለት መኾኗን ከሚያስገነዝቡ ትምህርቶች በተጨማሪ የደጋግ አባቶችን መንፈሳዊ ታሪክ፣ የወረሱትን ሰማያዊ ሕይወትና ያገኙትን ዘለዓለማዊ ሐሤት መሠረት በማድረግ እኛ ምእመናንም እንደ አባቶቻችን ለመንግሥተ ሰማያት በሚያበቃ ክርስቲያናዊ ምግባር ጸንተን መኖር እንደሚገባን የሚያተጋ ቃለ እግዚአብሔር ይቀርባል፡፡

በዕለቱ የሚነበበው የወንጌል ክፍል (ሉቃ. ፲፪፥፴፪-፵፩) የሰው ልጅ ዓለም የሚያልፍበትን ወይም ራሱ የሚሞትበትን ቀን አያውቅምና ዘወትር በክርስቲያናዊ ምግባር ጸንቶ መኖር እንደሚገባው፤ እንደዚሁም በዚህ ምድር ሳለ ለሥጋው የሚጠቅም ኃላፊ ጠፊ ሀብት ከመሰብሰብ ይልቅ ለነፍሱ የሚበጅ የጽድቅ ሥራን ማብዛትና የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ የሚያበቃ ክርስቲያናዊ ምግባርን መያዝ እንደሚጠበቅበት፤ በዚህም ሰማያዊውን መንግሥት ለመውረስ እንደሚቻለው የሚያስረዳ መልእክት አለው፡፡

እንግዲህ እንደ ታዘዝነው ነገ ለሚያልፍና ለሚጠፋ ምድራዊ ጉዳይ መጨነቃችንንና እርበርስ መገፋፋታችንን ትተን እግዚአብሔር አምላካችን ለፍርድ ሲመጣ ሰማያዊ ዋጋ ለመቀበልና የማያልፈውን መንግሥቱን ለመውረስ በሚያበቃን ክርስቲያናዊ ምግባር እንጽና፡፡ ‹‹ክርስቲያናዊ ኑሮ በዘመነ አስተምሕሮ›› ማለትም ይኸው ነው፡፡

የቀደመ በደላችንን ቈጥሮ ሳያጣፋን ዕድሜ ለንስሐ ሰጥቶ እስከ ዛሬ ድረስ የጠበቀን፤ ይቅርታ፣ ርኅራኄ፣ ቸርነት የባሕርዩ የኾነው አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር እንደ ቸርነቱ ዘለዓለማዊ መንግሥቱን ለመውረስ ያብቃን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ብፁዕ አቡነ ኤልያስ፣ ቤተ ክርስቲያንን ከነጣቂ ተኩላዎች መጠበቅ እንደሚገባ አሳሰቡ

ታኅሣሥ ፱ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

ብፁዕ አቡነ ኤልያስ የጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ

የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ከነጣቂ ተኩላዎች መጠበቅ እንደሚገባ ብፁዕ አቡነ ኤልያስ የጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ አሳሰቡ፡፡

ብፁዕነታቸው ይህን መልእክት ያስተላለፉት በጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከት በዐርባ ምንጭ ከተማ በደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን በተካሔደው የፀረ ተሐድሶ ጉባኤ ላይ ተገኝተው ‹‹እናንተ ግን ክፉውን ከመካከላችሁ አውጡ፡፡ በውጭ ባሉት ግን እግዚአብሔር ይፈርድባቸዋል›› (፩ኛ ቆሮ. ፭፥፲፫) በሚል ኃይለ ቃል ትምህርተ ወንጌል በሰጡበት ወቅት ነው፡፡

የተሐድሶ መናፍቃን ሴራ በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ላይ እየፈጠረ ያለው መለያየት ከፍተኛ መኾኑን የጠቆሙት ብፁዕነታቸው የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮችም ኾኑ ምእመናን ስልታዊ እንቅስቃሴያችንን አጠናክረን በትጋት መቀጠል እንዳለብን አስገንዝበዋል፡፡

የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ለማፋለስ፣ የአገርን አንድነትና የምእመናንን ሰላም ለማደፍረስ የሚንቀሳቀሱ መናፍቃንን አውግዛ በመለየት ቤተ ክርስቲያን ሓላፊነቷን በመወጣት ላይ እንደምትገኝ ያስታወሱት ብፁዕነታቸው መናፍቃኑ ከስሕተታቸው የሚመለሱ ከኾነ መክራ፣ አስተምራ እንደምትቀበላቸውም አስረድተዋል፡፡

ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ፣ ከኅዳር ፩-፲፭ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም፤ ገጽ ፩፡፡

ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል፣ መናፍቃንን አወገዙ

ታኅሣሥ ፩ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል የከፋ ሸካ ቤንች ማጂ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና የሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ሓላፊ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የከፋ ሸካ ቤንች ማጂ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና የሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ሓላፊ ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል፣ በአህጉረ ስብከታቸው የተሐድሶ ኑፋቄን ሲያስተምሩ የተገኙ መናፍቃንን ከቤተ ክርስቲያን ኅብረት ለዩ፡፡

ተወግዘው የተለዩት ግለሰቦች ‹ምስሉ ፈረደ›፣ ‹ፍጥረቱ አሸናፊ›፣ ‹ያሬድ ተፈራ›፣ ‹በኃይሉ ሰፊው› እና ‹እኩለ ሌሊት አሸብር› እንደሚባሉ፤ ከእነርሱ መካከልም ምስሉ ፈረደ እና ፍጥረቱ አሸናፊ መዓርገ ቅስና፤ ያሬድ ተፈራ እና እና በኃይሉ ሰፊው መዓርገ ዲቁና እንደ ነበራቸውና ሥልጣነ ክህነታቸው እንደ ተያዘ፤ የሰንበት ት/ቤት አገልጋይ የነበረውን እኩለ ሌሊት አሸብርን ጨምሮ ከዚህ በኋላ ዅሉም ግለሰቦች ከቤተ ክርስቲያን ኅብረት እንደ ተለዩና ‹አቶ› ተብለው እንደሚጠሩ ብፁዕነታቸው በሰጡት መግለጫ አስታውቀዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል ታኅሣሥ ፩ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም ለማኅበረ ቅዱሳን ብሮድካስት አገልግሎት በሰጡት መግለጫ እንዳስታወቁት ግለሰቦቹ ተወግዘው እንዲለዩ የተደረገው የኑፋቄ ትምህርት በማስተማር ሕዝበ ክርስቲያኑን ሲያደናግሩ ከመቆየታቸው ባሻገር ራሳቸውን ‹ተሐድሶ› ብለው በመሰየም ከቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ጋር የሚቃረን ትምህርት ሲሰጡ በማስረጃ በመረጋገጡ ነው፡፡

ተወግዘው ከተለዩ ግለሰቦች መካከል አምስቱ (ከግራ ወደ ቀኝ፡- ምስሉ ፈረደ፣ ፍጥረቱ አሸናፊ፣ ያሬድ ተፈራ፣ እኩለ ሌሊት አሸብር እና በኃይሉ ሰፊው)

በመጨረሻም እግዚአብሔር አምላክ የሰዉን ልጅ ድኅነት እንጂ ጥፋቱን የማይፈቅድ መኾኑን ያስታወሱት ብፁዕነታቸው ለብዙኃኑ ድኅነት ሲባል ጥቂቶችን አውግዞ መለየት የቤተ ክርስቲያን ሥርዓት መኾኑን አስረድተዋል፡፡ አያይዘውም የግለሰቦቹን ቃለ ውግዘት ለቅዱስ ሲኖዶስ እንደሚያቀርቡ በመጥቀስ ተወግዘው የተለዩትም ይኹን በማስጠንቀቂያ ላይ የሚገኙ ግለሰቦች ከስሕተታቸው ተመልሰው ንስሐ ቢገቡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንደምትቀበላቸው አሳስበዋል፡፡

የሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት በቍጥር 148/11/2010፣ በቀን 01/03/2010 ዓ.ም በጻፈው ደብዳቤ በተሐድሶ ኑፋቄ ውስጥ ኾነው ሕዝበ ክርስቲያኑን እያደናገሩ የሚገኙ ቀሳውስትን፣ ዲያቆናትንና ምእመናንን በአጠቃላይ የዐሥራ ሦስት ግለሰቦችን ስም በመጥቀስ ቀሳውስቱና ዲያቆናቱ ከክህነት አገልግሎት፤ ምእመናኑ ደግሞ ከቤተ ክርስቲያን አባልነት መታገዳቸውን ያሳወቀ ሲኾን፣ በደብዳቤው ከተጠቀሱ ግለሰቦች መካከልም ምስሉ ፈረደ እና ፍጥረቱ አሸናፊ ይገኙበታል፡፡

በተያያዘ ዜና የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ጽ/ቤት በቀን 22/03/2010 ዓ.ም ለ15ቱም የሀገረ ስብከቱ ወረዳ ቤተ ክህነት ጽ/ቤቶች በላከው ደብዳቤ መ/ር አዲስ ይርጋለም፣ ቀሲስ ካሡ ተካ፣ መ/ር ዓይነኵሉ ዓለሙ፣ መ/ር ኢሳይያስ ጌታቸው እና መ/ር ጎርፉ ባሩዳ የተባሉ አምስት አገልጋዮች በቤተ ክርስቲያን ዐውደ ምሕረትም ኾነ በሌላ ቦታ ምንም ዓይነት አገልግሎት እንዳይሰጡ አግዷቸዋል፡፡

ጾመ ነቢያት

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ኅዳር ፲፬ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

እግዚአብሔር አምላካችን ዓለምን ለማዳን ሲል የሰውን ሥጋ መልበሱን፣ ከእናቱ ቅድስት ድንግል ማርያም ጋር ወደ ግብጽ ግብር መሰደዱን፣ በባሕረ ዮርዳኖስ መጠመቁን፣ በትምህርቱ ብርሃንነት ጨለማውን ዓለም ማብራቱን፣ ለሰው ልጆች ድኅነት ሲል ልዩ ልዩ ዓይነት መከራ መቀበሉን፣ መሰቀሉን፣ መሞቱን፣ ከሙታን ተለይቶ መነሣቱን፣ ማረጉንና ዳግም ለፍርድ የሚመጣ መኾኑን በአጠቃላይ የማዳን ሥራውን በየዘመናቱ የተነሡ ቅዱሳን ነቢያት በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝተው አስቀደመው በትንቢት ተናግረዋል፡፡ ትንቢቱ ተፈጽሞ ለመመልከትም ‹‹አንሥእ ኃይለከ ፈኑ እዴከ፤ ኃይልህን አንሣ፤ እጅህን ላክ›› እያሉ በጾም በጸሎት ተወስነው አምላክ ሰው ኾኖ ዓለምን የሚያድንበትን ጊዜ በቀናት፣ በሳምንታት፣ በወራትና በዓመታት እያሰሉ ሲጠባበቁ ቆይተዋል፡፡ የእግዚአብሔርን ሰው መኾን ሲጠባበቁ የኖሩት የነቢያት ትንቢትና ጸሎትም በእግዚአብሔር ሰው መኾን ፍጻሜ አግኝቷል፡፡

ይህን ምሥጢር በማሰብ በየዓመቱ ከኅዳር ፲፭ ቀን ጀምሮ እስከ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ልደት ዋይዜማ ድረስ እንድንጾም አባቶቻችን መምህራነ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ሠርተውልናል፡፡ ይህ ጾም፣ ከሰባቱ አጽዋማት አንዱ ሲኾን፣ በስያሜም ‹‹ጾመ ነቢያት (የነቢያት ጾም)›› እየተባለ ይጠራል፡፡ ወቅቱ ለአዳም የተነገረው የድኅት ተስፋ የተፈጸመበት ስለ ኾነም ‹‹ጾመ አዳም (የአዳም ጾም)›› ይባላል፡፡ ስለ እግዚአብሔር ሰው መኾን በስፋት ትምህርተ ወንጌል የሚሰጥበት ወቅት በመኾኑም ‹‹ጾመ ስብከት (የስብከት ጾም)›› የሚል ስያሜ ተሰጥቶታል፡፡ የጾሙ መጨረሻ (መፍቻ) በዓለ ልደት በመኾኑ ደግሞ ‹‹ጾመ ልደት (የልደት ጾም)›› በመባል ይታወቃል፡፡ በተጨማሪም ‹‹ጾመ ሐዋርያት››  እየተባለ ይጠራል፡፡ ምክንያቱም ቅዱሳን ሐዋርያት ‹‹በዓለ ትንሣኤን ዐቢይ ጾምን ጾመን እናከብረዋለን፤ በዓለ ልደትንስ ምን አድርገን እናከብረዋለን?›› በማለት ነቢያት በጾሙበት ማለት ከልደተ ክርስቶስ በፊት ባለው ወቅት ጾመዋልና፡፡

በሌላ አጠራር ይኸው ጾመ ነቢያት ‹‹ጾመ ፊልጶስ (የፊልጶስ ጾም)›› በመባል ይታወቃል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ፊልጶስ በአፍራቅያ እና አውራጃዋ ዅሉ እየተዘዋወረ በጌታችን አምላካችንና ድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ወንጌልን በማስተማር፣ ድንቅ ድንቅ ተአምራትን በማድረግ ብዙዎችን ወደ አሚነ እግዚአብሔር ሲመልስ ቆይቶ ትምህርቱን በማይቀበሉ የአፍራቅያ ሰዎች አማካይነት በሰማዕትነት ዐርፏል፡፡ ደቀ መዛሙርቱ ሥጋውን ሊቀብሩ ሲሉም ተሰወረባቸው፡፡ በዚህ ጊዜ በዓት ዘግተው፣ ሱባዔ ገብው፣ በጾም በጸሎት ተወስነው የሐዋርያውን ሥጋ ይመልስላቸው ዘንድ እግዚአብሔርን ቢለምኑት ልመናቸውን ተቀብሎ ሱባዔ በያዙ በ፫ኛው ቀን የቅዱስ ፊልጶስን ሥጋ (በድን) መልሶላቸው በክብር አሳርፈውታል፡፡ ደቀ መዛሙርቱ የሐዋርያውን ሥጋ ካገኙ በኋላ እስከ ጌታችን ልደት ድረስ ጾመዋል፡፡ ስለዚህም ጾመ ነቢያት፣ ‹‹ጾመ ፊልጶስ›› እየተባለ ይጠራል፡፡

ከዚሁ ዅሉ ጋርም ወልደ አምላክ ክርስቶስን በግብረ መንፈስ ቅዱስ እንደምትፀንሰው፣ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ካበሠራት በኋላ ‹‹ሰማይና ምድር የማይወስኑትን አምላክ ፀንሼ ምን ሠርቼ እወልደዋለሁ?›› በማለት ጌታችንን ከመውለዷ አስቀድማ እመቤታችን ጾማዋለችና ይህ ጾም ‹‹ጾመ ማርያም›› በመባልም ይታወቃል፡፡ በአጠቃላይ በዚህ በጾመ ነቢያት፣ ነቢያትም ሐዋርያትም፣ ቀደምት አባቶቻችንም ጾመው በረከት አግኝተውበታል፡፡ እኛ ምእመናንም የነቢያት፣ የሐዋርያት፣ የጻድቃንና የሰማዕታት አምላክ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፣ ከቅዱሳን ነቢያትና ሐዋርያት በረከት እንዲያሳትፈን በዚህ በጾመ ነቢያት ወቅት በጾም በጸሎት ተወስነን እግዚአብሔርን ልንማጸነው ይገባናል፡፡ 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡ 

ምንጭ፡ 

  • ፍትሐ ነገሥት ንባቡና ትርጓሜው፣ አንቀጽ ፲፭፡፡ 
  • ጾምና ምጽዋት (፳፻፩ ዓ.ም)፣ ዲያቆን ቃኘው ወልዴ፤ ገጽ ፵፯ – ፶፡

በአውሮፓ የሕፃናት እና ታዳጊዎች ሥርዓተ ትምህርት ተመረቀ

በእንግሊዝ ንዑስ ማእከል

ኅዳር ፲፫ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

በምረቃ ሥርዓቱ ላይ የተገኙ የሰሜን ምዕራብ አውሮፓ ሀገረ ስብከት ሠራተኞች እና ካህናት በከፊል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰ/ት/ቤ/ማ/መ/ ማኅበረ ቅዱሳን አውሮፓ ማእከል የተተኪ ትውልድ ሥልጠና ክፍል አስተባባሪነት የተዘጋጀ ከኢትዮጵያ ውጪ የሚኖሩ ሕፃናት እና ታዳጊዎችን ለማስተማር የሚያግዝ ሥርዓተ ትምህርት በእንግሊዝ አገር በለንደን ከተማ በደብረ ገነት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ኅዳር ፫ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም ተመረቀ፡፡

በምረቃ ሥርዓቱ ላይ የሰሜን ምዕራብ አውሮፓ ሀገረ ስብከት ሠራተኞች፣ ከየአብያተ ክርስቲያናት የመጡ ካህናት፣ የሰንበት ት/ቤት አባላት፣ የየአብያተ ክርስቲያናት ተወካዮች፣ የአካባቢው ምእመናንና በማኅበረ ቅዱሳን አውሮፓ ማእከል የእንግሊዝ ንዑስ ማእከል አባላት ተገኝተዋል፡፡

መርሐ ግብሩ በሊቀ አእላፍ ቆሞስ አባ አሮን ሳሙኤል በሰሜን ምዕራብ አውሮፓ ሀገረ ስብከት የሰ/ት/ቤ/ማደራጃ ክፍል ሓላፊ በጸሎት የተከፈተ ሲኾን፣ የሀገረ ስብከቱ ዋና ጸሐፊ ቀሲስ በለጠ የእንኳን ደኅና መጣችሁ መልእክት አስተላልፈው የሥርዓተ ትምህርቱን ምረቃና አጠቃላይ ዝግጅት አስተዋውቀዋል፡፡

ዶ/ር በላቸው ጨከነ በማኅበረ ቅዱሳን የአውሮፓ ማእከል ምክትል ሰብሳቢ እና የሥርዓተ ትምህርቱ ዝግጅት አስተባባሪም የሥርዓተ ትምህርቱ የዝግጅት ሒደት፣ ዓላማ፣ አስፈላጊነት፣ ይዘት እና ቀጣይ ሥራዎችን በተመለከተ ባቀረቡት ገለጻ በሥርዓተ ትምህርት ዝግጅቱ ከሠላሳ የሚበልጡ የቤተ ክርስቲያን ልጆች መሳተፋቸውን አመላክተዋል፡፡

ዶ/ር በላቸው እንዳብራሩት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰሜን ምዕራብ አውሮፓ ሀገረ ስብከት ፈቃድ የተጀመረው የሕፃናትና ታዳጊዎች የሥርዓተ ትምህርት ዝግጅት ከሁለት ዓመታት በላይ የወሰደ ሲኾን፣ ዝግጅቱ ከመጀመሩ አስቀድሞም ከሦስት መቶ በላይ የሚኾኑ በእንግሊዝ አገር የሚኖሩ ምእመናን የተሳተፉበት የየአብያተ ክርስቲያናት ተሞክሮ፣ የልጆች የቋንቋ ክህሎት እና የቤተ ክርስቲያን ትምህርት ደረጃ፣ እንደዚሁም ወላጆች የተሳተፉበት በችግሮች እና የመፍትሔ አቅጠጫዎች ዙሪያ ያተኮረ የመነሻ ጥናት ተደርጓል፡፡

ጥናቱን መሠረት በማድረግም ለወደፊት የሚመለከታቸውን አካላት ዅሉ ለማሳተፍ የሚያስችል ጥናትና ምክረ ሐሳብ (ፕሮፖዛል) ለሰሜን ምዕራብ አውሮፓ ሀገረ ስብከት ቀርቦ የነበረ ሲኾን፣ የሀገረ ስብከቱ አስተዳደር ጉባኤም የቀረበውን ጥናትና ምክረ ሐሳብ ተቀብሎ በሀገረ ስብከቱ ሥር በሚገኙ አገሮች የወላጆች ኮሚቴ እንዲዋቀር ወስኗል፡፡ ለዚህም የሥራ መመሪያ ተዘጋጅቶ ለየአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት መላኩ ተገልጿል፡፡

እንደ ዶ/ር በላቸው ጨከነ ገለጻ ወጥ የኾነ ሥርዓተ ትምህርት አለመኖር በአውሮፓ የሚኖሩ ታዳጊ ሕፃናትን ለማስተማር ከባድ ከሚያደርጉት ኹኔታዎች ዐቢይ ምክንያት ሲኾን፣ ይህን በመገንዘብ የሰሜን ምዕራብ አውሮፓ ሀገረ ስብከት ባወጣው የሥራ መመሪያ መሠረት በማኅበረ ቅዱሳን አውሮፓ ማእከል የተተኪ ትውልድ ሥልጠና ክፍል ባለሙያዎችን በመመደብ ሥራውን እንዲጀምር ተደርጓል፡፡

ከአምስት እስከ ዘጠኝ ዓመት የዕድሜ ክልል ውስጥ ለሚገኙ ሕፃናትና ታዳጊዎች ታስቦ የተዘጋጀው ሥርዓተ ትምህርቱ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ ትምህርተ ሃይማኖት፣ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን፣ የአማርኛ ቋንቋ እና የመዝሙር ጥናት የተሰኙ አምስት የትምህርት ዘርፎችን ያካተተ ሲኾን፣ የትምህርቶቹ አርእስትና ይዘቶችም በቤተ ክርስቲያን የሚከበሩ በዓላትንና ወቅቶችን መሠረት በማድረግ የተዘጋጁ ናቸው፡፡

የሥርዓተ ትምህርቱ ጥራዞች

በቀጣይነትም በአውሮፓ ማእከል አስተባባሪነት የሕፃናት እና ታዳጊዎች ክፍልን በመላው አውሮፓ በሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት ለማቋቋምና ለማጠናከር፣ ለመምህራን ሥልጠና ለመስጠት፣ በየአገሩ የወላጆች ኮሚቴን ለማቋቋም እና ሥርዓተ ትምህርቱን በየአጥቢያው ለማዳረስ መታቀዱን ዶ/ር በላቸው ጨከነ አስረድተዋል፡፡

‹‹የእኛ ትወልድ፣ ነገ በመላው ዓለም ለምትኖረው ቤተ ክርስቲያን ድልድይ ነው፤›› ያሉት ዶ/ር በላቸው ጨከነ ለሥርዓተ ትምህርቱና ለሌሎችም ዕቅዶች ተግባራዊነት የሚመለከታቸው የቤተ ክርስቲያን አካላትና ምእመናን በትጋት ሊሠሩ እንደሚገባ በማሳሰብ መልእክታቸውን አጠቃለዋል፡፡

በምረቃ ሥርዓቱ ላይ የተገኙ ካህናትና ምእመናንም በዚህ ዝግጅት የተሳተፉ ወገኖችን ከማመስገን ጀምሮ ብዙ ጠቃሚ አስተያየት ሰጥተዋል፡፡ ለአብነትም ሊቀ አእላፍ ቆሞስ አባ አሮን ሳሙኤል በሰሜን ምዕራብ አውሮፓ ሀገረ ስብከት የሰ/ት/ቤ/ማደራጃ ክፍል ሓላፊ ዝግጅቱ አስፈላጊና ወቅታዊ መኾኑን ጠቅሰው በሕፃናት ላይ የሚሠራ ሥራ መሠረታዊ ለውጥ ለማምጣት የላቀ ጠቀሜታ እንዳለው ተናግረዋል፡፡

‹‹ይህ ሥራ ችግኝ ተከላ ነው›› ያሉት የለንደን ደብረ ገነት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ መልአከ ገነት ቀሲስ ከፍያለው አስቻለው በበኩላቸው ሕፃናትን የማስተማር አገልግሎት ለበርካታ ዓመታት በአእምሯቸው ሲመላለስ እንደ ቆየ አውስተው ‹‹ዝግጅቱ የልጆቻችንን ጥያቄ የሚመልስልን በመኾኑ ከአሁን በኋላ ዅላችንም በሓላፊነት ልንሠራበት ይገባል›› ሲሉ አሳስበዋል፡፡

‹‹በውጪ አገር ይህን ያህል ዓመት ስንኖር ዛሬ ገና ስለ ልጆቻችንን ማሰብ በመጀመራችን ደስ ብሎኛል›› በማለት ደስታቸውን የገለጹት ሊቀ ሊቃውንት ገብረ ሥላሴ ዓባይም በሰሜን ምዕራብ አውሮፓ ሀገረ ስብከት የስብከተ ወንጌል ክፍል ሓላፊ፣ ይህ ዝግጅት እንዲፈጸም ላደረገው ለእግዚአብሔር ምስጋና ካቀረቡ በኋላ ለሥራው ተግባራዊነትም ዅሉም ጠንክሮ መሥራት እንደሚገባው አስገንዝበዋል፡፡

በሊቨርፑል ከተማ የመካነ ቅዱሳን አቡነ ተክለ ሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ ሊቀ ትጉሃን ቀሲስ ብርሃኑ ደሳለኝ ደግሞ ቤተ ክርስቲያናችን ያላትን ብዙ ሀብት በሚገባ እየተጠቀምንበት እንዳልኾነ አስታውሰው ዝግጅቱ ተጠናቆ ለምረቃ በመብቃቱም ‹‹ቤተ ክርስቲያናችን እንኳን ደስ ያላት! እናንተም እንኳን ደስ ያላችሁ!›› በማለት የተሰማቸውን ደስታ ገልጸዋል፡፡

መጋቤ ሐዲስ ክብረት የለንደን ደብረ ገነት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን አገልጋይም እንደዚሁ ይህ ዝግጅት ለሕፃናት መንፈሳዊ ሕይወት ከሚኖረው ጠቀሜታ ባሻገር ሕፃናት ከወላጆች ጋር እንዲግባቡ የሚያግዝ ሥራ መኾኑንም መስክረዋል፡፡ በተመሳሳይ መልኩ አንዳንድ ምእመናንም ለሥራው ውጤታማነት የሚጠቅሙ ገንቢ አስተያየቶችን ሰጥተዋል፡፡

በመጨረሻም የተዘጋጁት የመምህራን መምሪያ እና የሥርዓተ ትምህርት መድብሎች ከየአጥቢያው ለመጡ የሰበካ ጉባኤ ተወካዮች ከተሰጡ በኋላ በሰሜን ምዕራብ አውሮፓ ሀገረ ስብከት ዋና ጸሐፊ ቀሲስ በለጠ መርዕድ የማጠቃለያ መልእክትና ጸሎተ ቡራኬ የምረቃ ሥርዓቱ ተጠናቋል፡፡

‹‹በመንገድ ላይ እንዳላጠፋህ በፊትህ መልአክ እሰዳለሁ፤›› (ዘፀ. ፴፫፥፫)፡፡

በመምህር ኢዮብ ይመኑ 

ኅዳር ፲፪ ቀን ፳፻፲ ዓ.

በረኃብ ምክንያት ከከነዓን ወደ ግብጽ የተሰደዱት የያዕቆብ ቤተሰቦች፣ በአባታቸው በያዕቆብ ምርቃት በግብጽ ምድር ቍጥራቸውም እጅግ እየበዛ መጣ፡፡ መብዛታቸውም ከ፲፪፻፹ – ፲፬፻፵፭ ቅድመ ልደተ ክርስቶስ የተነሣውን፣ ዮሴፍን የማያውቀውን ንጉሥ አስፈራው (ዘፀ. ፩፥፰)፡፡ ንጉሡም ጠላት ይኾኑብናል ያም ባይኾን ጠላት ቢነሣብን አብረው ይወጉናል በሚል ፍርኃት፣ አገዛዙን አጸናባቸው፡፡ በከባድ ሥራ እየጠመደ በጭካኔ ጡብ እያስገነባ ፊቶም፣ ራምሴ፣ ዖን የተባሉ ታላላቅ ከተሞችን አሠራቸው፡፡ ኖራ እያስወቀጠ፣ ጭቃ እያስረገጠ በሥራ ደክመው ልጅ እንዳይወልዱ ጉልበታቸውን አደከማቸው፡፡ በጅራፍ እየገረፈ መከራ አጸናባቸው፡፡ ይህን ቢያደርግም ጉልበታቸው እየበረታ፣ ከእርሱ መከራ የአባቶቻቸው ምርቃትና ቃል ኪዳን እየረታ አሁንም በዙ፡፡ ንጉሡም ወንድ ሲወለድ በመግደል እስራኤልን ለመቆጣጠር ሞከረ፡፡ ነገር ግን የመከራው ብዛት የሕዝቡም ጩኸት የራሔልም ዕንባ የሕዝቡን መከራ ቅድመ እግዚአብሔር እንዲደርስ አደረገው፡፡

በግብጽ ምድር በመከራ የኖሩት እስራኤላውያን፣ በፈርዖንና በሠራዊቱ ላይ ከደረሱ ፱ መቅሠፍቶች፣ ፲ኛ ሞተ በኵር እና ፲፩ኛ ስጥመተ ባሕር በኋላ በእግዚአብሔር ፈቃድ፣ በቅዱስ ሚካኤል ተራዳኢነትና በሙሴ ጸሎት በተአምራት ከግብጽ ምድር ወጥተው ወደ ርስታቸው ከነዓን ገብተዋል፡፡ ‹‹በመንገድ ላይ እንዳላጠፋህ በፊትህ መልአክ እሰዳለሁ፤›› (ዘፀ. ፴፫፥፩-፫) ተብሎ እንደ ተጻፈው፤ ከመከራ የወጡትን እስራኤል በጉዟቸው ከሚገጥማቸው መሰናከል እየጠበቀ፣ በመንገድ ላይ እንዳይጠፉ እያማለደ፣ በምሕረት እየታደገ፣ ከጠላት ጋር ሲዋጉም አብሮ እየቀደመ፣ ከዲያብሎስ ተንኮል እየሰወረ እግዚአብሔር ወዳዘጋጀላቸው ሥፍራ ያስገባቸው የእግዚአብሔር መልአክ የቅዱስ ሚካኤል መታሰቢያ በዓል በየዓመቱ ኅዳር ፲፪ ቀን በቤተ ክርስቲያናችን ይከበራል፡፡

እግዚአብሔር የሰው ልጆችን ድካም የሚያውቅ አምላክ ነው፡፡ የሰው ልጅ ደግሞ የእግዚአብሔርን ውለታ የሚዘነጋ፣ የተደረገለትንም የሚረሳ፣ ፊቱ ባለ ነገር ላይ ብቻ የሚጨነቅ፣ ነገ በሚመጣው ብቻ የሚጠበብ እንጂ የትናንትና ታሪኩን አስቦ እግዚአብሔርን የሚያመሰግን ባለመኾኑ፣ የተደረገለትን ውለታ እንዳይረሳ ይልቁን እግዚአብሔርን እንዲያመሰግን እንደዚሁም ያለፉት ሥራዎቹ እንዳይረሱ መታሰቢያን ሰጥቶናል፡፡ የቅዱሳን በመታሰቢያ በዓላት እኛን እንድንድን ለመርዳትና ለማገዝ የተሠሩ ሥርዓቶች ናቸው፡፡ መጽሐፍ ‹‹መታሰቢያህም ለልጅ ልጅ ነው … ይህ ለሚመጣ ትውልድ ይጻፍ፡፡ የሚፈጠርም ሕዝብ ለእግዚአብሔር ዕልል ይላል›› (መዝ. ፻፩፥፲፪) እንዳለ የቅዱሳን በዓል መታሰቢያነቱ የእግዚአብሔርን ሥራ ለማድነቅ ለማመስገን ነው፡፡ ተጠቃሚዎቹ ደግሞ እኛ ምእመናን ነን፡፡ ከዚህም ባሻገር መጪውን ትውልድ ወደ እግዚአብሔር ማቅረቢያ፣ ለነገ መንፈሳዊ ሕይወት ማዘጋጃ፣ የበረከትም ማግኛ ይኾናል – መታሰቢያ፡፡

በመጽሐፍ ቅዱስ እንደ ተመዘገበው የዮርዳኖስን የሞላ ውኃ በእግዚአብሔር ተአምራት ተቋርጦ በደረቅ መሻገራቸው ለማሰብ ኢያሱ እስራኤላውያንን ‹‹በአምላካችሁ በእግዚአብሔር ታቦት ፊት ወደ ዮርዳኖስ መካከል እለፉ፡፡ ከእናንተም ሰው ዅሉ በእስራኤል ልጆች ነገድ ቍጥር በጫንቃው ላይ አንድ አንድ ድንጋይ ከዚያ ይሸከም፡፡ ይህም በመካከላችሁ ምልክት ይኾናል ልጆቻችሁም በሚመጣ ዘመን ‹የእነዚህ ድንጋዮች ነገር ምንድር ነው?› ብለው ሲጠይቁአችሁ እናንተበእግዚአብሔር ቃል ኪዳን ታቦት ፊት የዮርዳኖስ ውኃ ስለ ተቋረጠ ነው፤ እነዚህ ድንጋዮች ለእስራኤል ልጆች ለዘለዓለም መታሰቢያ ይኾናሉ› ትሏቸዋላችሁ፤›› ብሏቸዋል (ኢያሱ ፬፥፬-፯)፡፡ ይህም መታሰቢያ ዕለታት ወይም በዓላት ወይም ምልክቶች ጥቅም እንዳላቸው ያስረዳናል፡፡ በእነዚህ ዕለታት፣ ሰው እግዚአብሔርን አመስግኖ፣ ከቅዱሳኑ በረከት አግኝቶ፣ ራሱን በቅድስና ሥፍራ አውሎ፣ ቅድስናን ተምሮ ለቅድስና የሚያበቃውን በረከት ያገኛል፡፡  እግዚአብሔር አምላካችን ሥራ የሠራበት፣ በጽኑ ተአምራት ሕዝቡን የታደገበት መንገድ እንደ ቀላል በዝምታ የሚታለፍ ሳይኾን መታሰቢያ የሚደረግለት በዓል ነው፡፡ ‹‹ተዝካረ ገብረ ለስብሐቲሁ፤ ለተአምራቱ መታሰቢያአደረገ፤›› (መዝ. ፻፲፥፬) ተብሎ እንደ ተጻፈ፡፡

ስለዚህም ኅዳር ፲፪ ቀን እግዚአብሔር በታላላቅ ተአምራት ሕዝቡን ነጻ ያወጣበት ዕለት በመኾኑ የመታሰቢያ በዓል ኾኗል፡፡ እግዚአብሔር በባሕርዩ የእርሱ ለኾኑት ቅዱሳን ክብርና ሞገስ የሚሰጥ አምላክ ነው፡፡ ሰዎች የእርሱ የኾኑትን እንዲያከብሩለት የሚፈልግ አምላክም ነው፡፡ ለዚህም ነው ‹‹እነሆም መጥተው በእግሮችህ ፊት ይሰግዱ ዘንድ እኔም እንደወደድኹህ ያውቁ ዘንድ አደርጋቸዋለሁ፤›› በማለት የተናገረው (ራዕ. ፫፥፱)፡፡ ወዳጆቹን ማክበር እግዚአብሔርን ማክበር ነው፡፡ እነርሱን ማሰብም እርሱን ማሰብ ነውና ነው፡፡ ‹‹የእግዚአብሔርን ቃል የተናገሯችሁን ዋኖቻችሁን አስቡ፡፡ የኑሮአቸውንም ፍሬ እየተመለከታችሁ በእምነት ምሰሏቸው›› ተብሎ እንደ ተጽፏልና (ዕብ. ፲፫፥፯)፡፡

ቅዱሳኑን መመልከት እግዚአብሔርን መመልከት ነው፡፡ ስለዚህም ይህ የከበረ ዕለት፣ እስራኤል በመንገድ ላይ እንዳይጠፉ በቅዱስ ሚካኤል ተራዳኢነት፣ ጥበቃና መሪነት ወዳዘጋጀላቸው ሥፍራ መግባታቸውን የምናስብበት በዓል ነው፡፡ ቤቱ የእርሱ ቢኾንም መታሰቢያነቱን ለወዳጆቹ፣ ደስ ላሰኙት ቅዱሳኑ እግዚአብሔር ይሰጣል (ኢሳ. ፶፮፥፬)፡፡ ልዩ ከኾነው ስሙ ጋር ስማቸው አብሮ እንዲነሣ ያደርጋል፡፡ አድሮባቸው ሥራ ሠርቷልና እንዲሁ አይተዋቸውም፤ እንዲታሰቡለት ያደርጋል እንጂ፡፡ በቤቱም በፊቱም እነርሱ ሲታሰቡና ሲከብሩ ደስ ይሰኛል፡፡ ምንጩም ፈቃጁም እርሱ ራሱ ነውና፡፡ ‹‹እግዚአብሔርን ለሚፈሩ፣ ስሙንም ለሚያስቡ የመታሰቢያ መጽሐፍ በፊቱ ተጻፈ፤›› እንዳለ ነቢዩ (ሚል. ፫፥፲፮)፡፡ ቅዱሳኑ ስሙን በፍጹም አስበዋልና እግዚአብሔር ደግሞ ስማቸው በሌሎች (በእኛ) እንዲታሰብ ፈቅዷል፡፡ ከዚህ አኳያ ከእስራኤል ዘሥጋ ነጻ መውጣት ጋር ‹‹ስሜ በእርሱ ስለ ኾነ›› (ዘፀ. ፳፫፥፳) የተባለለት ቅዱስ ሚካኤል፣ በየዓመቱ ኅዳር ፲፪ ቀን መታሰቢያው ይከበራል፡፡

‹‹የእግዚአብሔር ሠራዊት አለቃ ኾኜ አሁን መጥቼአለሁ›› (ኢያሱ ፭፥፲፬) በማለት መልአኩ እንደ ተናገረው ኢያሱና እስራኤላውያንን የረዳቸው፣ ያጸናቸው እርሱ ቅዱስ ሚካኤል ነው፡፡ ዲያብሎስ በተንኮል የሙሴን መቃብር አሳይቶ ሕዝቡን በአምልኮ ጣዖት ሊጥል ሲያደባ በጣዖት ወድቀው እግዚአብሔርን በድለው እንዳይጠፉ ከፊታቸው ቀድሞ ከዲያብሎስ ስውር ሤራ የጠበቃቸው ቅዱስ ሚካኤል ነው፡፡ ‹‹የመላእክት አለቃ ሚካኤል ግን ከዲያብሎስ ጋር በተከራከረ ጊዜ ስለ ሙሴ ሥጋ ሲነጋገር ‹ጌታ ይገሥፅህ› አለው እንጂ የስድብን ፍርድ ሊናገረው አልደፈረም፤›› እንዲል (ይሁዳ፣ ቍ. ፱)፡፡ ዳግመኛም ቀኑን በደመና ዓምድ ከበረኃው ዋዕይ እየጋረደ፣ ሌሊቱን በብርሃን ዓምድ ጨለማውን እያስወገደ፣ ከመሰናክል እያዳነ ከመከራ እየጠበቀ እስራኤልን ነጻ አውጥቷቸዋልና ለቅዱስ ሚካኤል መታሰቢያ በዓል ተደርጎለታል (ዘፀ. ፳፫፥፳፤ መዝ. ፴፫፥፯)፡፡

በዘመነ ኦሪት የሶምሶንን አባት እና እናት ልጅ እንደሚወልዱ ባበሠራቸው ጊዜ ማኑሄ፣ ‹‹ነገርህ በደረሰ ጊዜ እንድናከብርህ ስምህ ማን ነው?›› (መሣ. ፲፫፥፲፯) በማለት የእግዚአብሔርን መልአክ መጠየቁ በምስጋና፣ በደስታ ቀናቸው ይህን ተአምራት ያሳያቸውን መልአክ ለማክበርና መታሰቢያ ለማድረግ ነበር፡፡ ይህም የቅዱሳንን በዓል የማበክበር ትውፊት ከጥንት ጊዜ ጀምሮ መኖሩን በሚገባ ያሳያል፡፡ የደስታ፣ የምስጋና ቃል የሚሰማበት ቀን ደግሞ ‹በዓል› ይባላል፡፡ መጽሐፍ ‹‹በዓል የሚያደርጉ ሰዎች የደስታ የምስጋና ቃል አሰሙ›› ይላልና (መዝ. ፵፩፥፭)፡፡ እግዚአብሔር በላያቸው ላይ አድሮ ሥራ የሠራባቸውን፣ ተአምራቱን የገለጸባቸውን ቅዱሳን መላእክት፣ ጻድቃንና ሰማዕታትን የመታሰቢያ በዓል እኛም በዚህ ዘመን በደስታና በምስጋና ማክበራንም ፍጹም አምላካዊና መንፈሳዊ መንገድ መኾኑን አምነን እንመሰክራለን፡፡ ‹‹ቀንን የሚያከብር ለጌታ ብሎ ያከብራል›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (ሮሜ. ፲፬፥፮)፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

አርዮስ እና መንፈቀ አርዮሳውያን በቤተ ክርስቲያን ላይ ያደረሱት ችግር – የመጨረሻ ክፍል

በቀሲስ ዶ/ር ምክረ ሥላሴ ገብረ አማኑኤል

ኅዳር ፲፪ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

፫. ከኒቅያ ጉባኤ በኋላ አርዮሳውያን እና መንፈቀ አርዮሳውያን

የኒቅያ ጉባኤ ከተፈጸመ ከሦስት ዓመት በኋላ ማለት በ፫፻፳፰ ዓ.ም የእስክንድርያው ሊቀ ጳጳስ እለእስክንድሮስ ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ፡፡ ሊቀ ጳጳስ እለእስክንድሮስ ከመሞታቸው አስቀድሞ በተናዘዙት ቃል መሠረት፣ በኒቅያው ጉባኤ የተዋሕዶ ጠበቃ የነበሩትና በኒቅያው ጉባኤ ትምህርተ ሃይማኖትን (ጸሎተ ሃይማኖትን) ያረቀቁት ታላቁ አትናቴዎስ በምትካቸው በጳጳሳት፣ በካህናትና በሕዝብ ሙሉ ድምፅ ተመርጠው የእስክንድርያ ፓትርያርክ ሆነው ተሾሙ፡፡ ፓትርያርክ አትናቴዎስ በኒቅያ ጉባኤ ጊዜ የአርዮስና የተከታዮቹን የክሕደት ትምህርት በመቃወም ባቀረቡት ክርክርና ለኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት መጠበቅ ባበረከቱት ተጋድሎ በምዕራብም ሆነ በምሥራቅ ባሉ አብያተ ክርስቲያናት ሁሉ ‹‹ታላቁ አትናቴዎስ›› እየተባሉ ይጠራሉ፡፡ አርዮሳውያን እና መንፈቀ አርዮሳውያን በኒቅያ ጉባኤ ከተወገዙ በኋላም በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ላይ ዘመቻቸውን ከበፊቱ አብልጠው ስለ ቀጠሉ፣ ታላቁ አትናቴዎስ በጽሑፍና በቃል ትምህርት ለእነዚህ መናፍቃን ምላሽ መስጠታቸውን እስከ ዕለተ ሞታቸው ድረስ አላቋረጡም ነበር፡፡

የኒቅያ ጉባኤ እንደ ተፈጸመ አርዮስ እና የአርዮስ ተከታዮች ሁሉ በንጉሡ በቈስጠንጢኖስ ትእዛዝ ወደ ግዞት ተልከው ነበር፡፡ በዚህ ጊዜ አርዮሳውያን የንጉሡንና የፖለቲካ ባለ ሥልጣኖችን ለመወዳጀትና የእነርሱን ድጋፍ ለማግኘት ይሯሯጡ ጀመር፡፡ ስለዚህም ከሁለት ዓመት በኋላ ቆስጣንዲያ በተባለችው በንጉሡ እኅት እና የንጉሡ ወዳጅ በነበረው በኒቆምዲያው ኤጲስ ቆጶስ አውሳብዮስ አማካይነት ብዙዎቹ አርዮሳውያን ከግዞት እንዲመለሱ ታላቅ ሙከራ ተደረገ፡፡ በዚህም ምክንያት አርዮስና አያሌ አርዮሳውያን ከግዞት ተመለሱ፡፡ ከዚህ ጊዜ ጀምሮ ቤተ ክርስቲያንን ያወካት የነገሥታቱ በሃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ መግባት ነበር፡፡ በጉባኤ ሲኖዶስ የተወገዘው አርዮስ ከውግዘት እንዲፈታና ወደ እስክንድርያ ተመልሶ በቤተ ክርስቲያን በየነበረው ሥልጣን አገልግሎቱን እንዲቀጥል ንጉሡ ለሊቀ ጳጳሱ ለአትናቴዎስ ትእዛዝ አስተላለፈላቸው፡፡ ንጉሡ ይህን ትእዛዝ ያስተላለፈው ‹‹አርዮስ ከክሕደቱ ተመልሷል›› ብለው ወዳጆቹ ያስወሩትን ወሬ በመስማትና ‹‹የአርዮስ የእምነት መግለጫ ነው›› ተብሎ የቀረበለትን ግልጽ ያልሆነ መረጃ በመመልከት ነበር፡፡ ነገር ግን ይህን መግለጫ አርዮስን ያወገዘው ሲኖዶስ መርምሮ ሲያጸድቀው ነበር – ከክሕደቱ መመለሱ የሚታወቀው፡፡

በ፫፻፳፱ ዓ.ም የአርዮስ ደጋፊ በነበረው በኒቆምዲያው ኤጲስቆጶስ አውሳብዮስ የተመራውና አርዮሳውያን በብዛት የነበሩበት ጉባኤ ተሰብስቦ ‹‹አርዮስ ከውግዘቱ ተፈቷል›› በማለት ወሰኑ፡፡ የውሳኔአቸውን ግልባጭ በማያያዝም አትናቴዎስ አርዮስን እንዲቀበለው ንጉሠ ነገሥቱ መልእክት አስተላለፈ፡፡ አትናቴዎስ ግን የንጉሡን ትእዛዝና የአርዮሳውያንን ጉባኤ ውሳኔ አልቀበልም አሉ፡፡ ያልተቀበሉበትንም ምክንያት በዝርዝር ለንጉሡ ጻፉ፡፡ አርዮሳውያንና መንፈቀ አርዮሳውያንም የአትናቴዎስን እምቢታ (የንጉሡን ትእዛዝ አለመቀበል) መነሻ በማድረግ አትናቴዎስን እና ሌሎች ኦርቶዶክሳውያን መሪዎችን ከንጉሠ ነገሥቱ ጋር ለማጣላት የተቻላቸውን ሁሉ ጥረት አደረጉ፡፡ አርዮስ ወደ እስክንድርያ ተመልሶ ወደ ቀድሞው የክህነት ሥልጣኑ እንዲመለስ ንጉሠ ነገሥቱ ቈስጠንጢኖስ ያዘዘውን ትእዛዝ አትናቴዎስ ባለመቀበላቸውና መንግሥት በአርዮስ ጉዳይ ጣልቃ መግባቱን በመቃወማቸው የተነሣም ንጉሠ ነገሥቱ እጅግ ተቈጥቶ ነበር፡፡

ፓትርያርክ አትናቴዎስ የአርዮስ መወገዝም ሆነ መፈታት የሚመለከተው ቤተ ክርስቲያንን እንጂ ቤተ መንግሥትን አለመሆኑን ገልጠው ከመጻፋቸውም በላይ፣ ‹‹በሲኖዶስ የተወገዘ በመንግሥት ሳይሆን በሲኖዶስ ነው መፈታት ያለበት›› እያሉ ይናገሩ ስለ ነበር ንጉሡ በዚህ እጅግ አልተደሰተም ነበር፡፡ ንጉሡ በአትናቴዎስ ላይ መቆጣቱን የሚያውቁ አርዮሳውያንም አትናቴዎስን በልዩ ልዩ የሐሰት ክሶች ይከሷቸው ጀመር፡፡ ከሐሰት ክሶቹም አንዱ ‹‹ከግብጽ ወደ ቊስጥንጥንያ ስንዴ እንዳይላክ አትናቴዎስ ከልክለዋል›› የሚል ሲሆን፣ ሌላው ደግሞ ‹‹በንጉሡ ላይ ለሸፈቱ ሽፍቶች አትናቴዎስ ስንቅና መሣሪያ ያቀብሉ ነበር›› የሚል ነበር፡፡ ሌሎችም ሞራልንና ወንጀልን የሚመለከቱ የሐሰት ክሶችም ቀርበውባቸዋል፡፡

ሆኖም ግን ንጉሠ ነገሥቱ ቈስጠንጢኖስ አትናቴዎስን ለመበቀል ጥሩ አጋጣሚ ስላገኘ በአትናቴዎስ ላይ የቀረቡት ክሶች በጉባኤ እንዲታዩ ትእዛዝ አስተላለፈ፡፡ ጉባኤውም በ፫፻፴፭ ዓ.ም በጢሮስ ከተማ ተካሔደ፡፡ አትናቴዎስም ማንንም ሳይፈሩ ወደ ጉባኤው ሔዱ፡፡ ጉባኤው እንደ ተጀመረም በአትናቴዎስ ላይ የቀረቡትን ክሶች መስማት ጀመረ፡፡ በዚህ ጉባኤ አብዛኞቹ አርዮሳውያን ስለነበሩ፣ አትናቴዎስ በተከሰሱባቸው ክሶች ሁሉ ነጻ ቢሆኑም በግፍ ወደ ግዞት ቦታ እንዲሔዱ ተፈርዶባቸው ትሬቭ (ፈረንሳይ ውስጥ የምትገኝ) ወደምትባል ቦታ ተጋዙ፡፡

፬. የአርዮስ ድንገተኛ ሞት

ፓትርያርክ አትናቴዎስን በግፍ ወደ ግዞት ቦታ እንዲሔዱ የፈረደባቸው የቂሣርያው ጉባኤ፣ ‹‹አርዮስ ተጸጽቶ ከክሕደቱ መመለሱን የሚያመለክት መጣጥፍ አቅርቧል›› በሚል ሰበብ አርዮስን ከግዝቱ ፈቶ ነጻ አወጣው፡፡ አትናቴዎስ ወደ ግዞት በመላካቸው አርዮሳውያን እና መንፈቀ አርዮሳውያን ምቹ ጊዜ አግኝተው ስለ ነበር አርዮስን ወደ ሀገሩ ወደ እስክንድርያ ለመመለስ ይሯሯጡ ጀመር፡፡ የአርዮስ ነጻ መውጣትም ንጉሡ በሚኖርበት በቊስጥንጥንያ በይፋ እንዲከበር በማሰብ አርዮስ በወዳጆቹና በደጋፊዎቹ ታጅቦ ወደ ቊስጥንጥንያ እንዲሔድ አደረጉ፡፡ በዚያም በሐዋርያት ቤተ ክርስቲያን ከቊስጥንጥንያው ሊቀ ጳጳስ ጋር እንዲቀድስና ወደ ክርስቲያን አንድነት መግባቱ በይፋ እንዲታወጅ ዝግጅት ተደርጎ ሳለ ሆዱን ሕመም ተሰምቶት ወደ መጸዳጃ ቤት ሔዶ በዚያው ቀረ፡፡ አርዮስ ስለ ዘገየባቸው ደጋፊዎቹ ሔደው ቢያዩት ሆድ ዕቃው ተዘርግፎ ሞቶ አገኙት፡፡ በዚህም ‹‹የእግዚአብሔር ቊጣና መቅሠፍት በአርዮስ ላይ ተገለጠ›› ተብሎ በብዙ ሰዎች ዘንድ ታመነ፡፡ ሆኖም በአርዮስ ሞት የተበሳጩ አንዳንድ የአርዮስ ደጋፊዎች የእግዚአብሔርን ፍርድ አይተው ከክሕደታቸው በመመለስ ፈንታ ‹‹አርዮስ የሞተው በመድኃኒት ተመርዞ ነው›› ብለው ማውራትና ማስወራት ጀመሩ፡፡

፭. አርዮሳውያን እና መንፈቀ አርዮሳውያን የኒቅያን ውሳኔ ለመቀልበስ ያደረጉት ዘመቻ

የእስክንድርያው ፓትርያርክ ታላቁ አትናቴዎስ የክርስቶስን አምላክነት የካደውን የአርዮስን ሞት የሰሙት ያለ ፍትሕ በግፍ በተጋዙበት ሀገር ሳሉ ነው፡፡ ታላቁ ቈስጠንጢኖስም ብዙ ጊዜ በሕይወት አልቆየም፡፡ ንጉሡ ታሞ ግንቦት ፳፩ ቀን ፫፻፴፯ ዓ.ም ከዚህ ዓለም በሞት ተለየ፡፡ ሦስቱ ልጆቹ ማለት ዳግማዊ ቈስጠንጢኖስ፣ ቆንስጣንዲያስ እና ቁንስጣ መንግሥቱን ለሦስት ተከፋፈሉት፡፡ ከሦስቱ ልጆቹ መካከል የምዕራቡን ክፍል ይገዙ የነበሩት ሁለቱ ማለት ኦርቶዶክሳውያኑ ዳግማዊ ቈስጠንጢኖስ እና ቁንስጣ ሲሆኑ፣ መናገሻ ከተማውን ቊስጥንጥንያ ላይ አድርጎ የምሥራቁን ክፍል ይገዛ የነበረው ደግሞ አርዮሳዊው ቆንስጣንዲያስ ነበር፡፡ ትልቁ ቈስጠንጢኖስ ከሞተ ከአንድ ዓመት በኋላ ኅዳር ፳፫ ቀን ፫፻፴፰ ዓ.ም አትናቴዎስ ተግዘውበት የነበረበትን ሀገር ይገዛ የነበረው ዳግማዊ ቈስጠንጢኖስ አትናቴዎስን ከተጋዙበት እንዲመለሱ አደረገ፡፡ አትናቴዎስ ከግዞት ወደ እስክንድርያ ሲመለሱም ሕዝቡ እጅግ ተደስቶ በዕልልታና በሆታ ተቀበላቸው፡፡ አቀባበሉም ለአንድ ተወዳጅ ንጉሠ ነገሥት የሚደረግ አቀባበል ዓይነት ነበር፡፡

ፓትርያርክ አቡነ አትናቴዎስ በአርዮሳውያንና በመንፈቀ አርዮሳውያን ነገሥታት ያለ ፍትሕ በግፍ ለአምስት ጊዜያት ያህል ሕይወታቸውን በግዞት ነው ያሳለፉት፡፡ በእስክንድርያ መንበረ ጵጵስና በፓትርያርክነት የቆዩት ለ፵፮ ዓመታት ቢሆንም፣ ፲፭ቱን ዓመታት ያሳለፉት በግዞትና በስደት ነበር፡፡ ፓትርያርክ አትናቴዎስ ከዕድሜያቸው አብዛኛውን ዘመን ያሳለፉት ከአርዮሳውያን ጋር በመታገልና በመዋጋት ነበር፡፡ አንድ ታሪክ ጸሓፊም ‹‹ሙሴ ለእስራኤል ሕዝብ ምድረ ርስትን ለማውረስ የጀመረውን ተግባር ከግቡ ሳያደርስ እንደ ተጠራ፣ አትናቴዎስም ከአርዮሳውያን ጋር ያደርጉ የነበረውን ትግል ሳይጨርሱ ነው ለሞት የተጠሩት፤›› በማለት የፓትርያርክ አትናቴዎስን ተጋድሎና የአገልግሎት ፍጻሜ ያስረዳሉ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ማስገንዘቢያ

የተወደዳችሁ የማኅበረ ቅዱሳን ድረ ገጽ ተከታታዮች! ‹‹አርዮስ እና መንፈቀ አርዮሳውያን በጥንት ቤተ ክርስቲያን ላይ ያደረሱት ችግር›› በሚል ርእስ በቀሲስ ዶ/ር ምክረ ሥላሴ ገብረ አማኑኤል የተዘጋጀው ይህ ጥናታዊ ጽሑፍ፣ በግንቦት ወር ፳፻፰ ዓ.ም ለማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማእከል መቅረቡን፤ እንደዚሁም በኅዳር ወር ፳፻፱ ዓ.ም በታተመው ፳፬ኛ ዓመት ቍጥር ፯ ሐመር መጽሔት፣ ከገጽ ፰ – ፲፬ ለንባብ መብቃቱን ለማስገንዘብ እንወዳለን፡፡

አርዮስ እና መንፈቀ አርዮሳውያን በቤተ ክርስቲያን ላይ ያደረሱት ችግር – ክፍል ሦስት

በቀሲስ ዶ/ር ምክረ ሥላሴ ገብረ አማኑኤል

ኅዳር ፲፩ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

በስብሰባው ላይ አርዮሳውያን በኒቆምዲያው ኤጲስቆጶስ አውሳብዮስ አማካይነት የሃይማኖት መግለጫ (confession of faith) አቀረቡ፡፡ የተሰበሰቡት አባቶች አብዛኛዎቹ በጩኸትና በቁጣ ድምፅ የእምነት መግለጫውን ተቃወሙት፡፡ ጽሑፉንም በእሳት አቃጠሉት፡፡ ከዚህ በኋላ የቂሣርያው አውሳብዮስ በሀገረ ስብከቱ በጥምቀት ጊዜ የሚጠመቁ ሁሉ የሚያነቡት የሃይማኖት ጸሎት (መግለጫ) አቀረበ፡፡ ይህ መግለጫ ከኒቅያው የሃይማኖት ጸሎት ጋር ተመሳሳይነት ስለነበረው ለጊዜው ተቀባይነትን አግኝቶ የነበረ ቢሆንም ነገር ግን ‹‹ዋሕደ ባሕርይ ምስለ አብ›› ወይም ‹‹ዘዋሕድ ምስለ አብ በመለኮቱ›› (omoousios) የሚለውን አገላለጽ ባለማካተቱ ጠንከር ባሉ ኦርቶዶክሳውያን ዘንድ ተቀባይነት አላገኘም፡፡ በስብሰባው ወቅት አርዮስ ትክክለኛ የእምነት አቋሙን እንዲገልጽ ተጠይቆ ‹‹ሀሎ አመ ኢሀሎ ወልድወልድ ያልነበረበት ጊዜ ነበረ፡፡ አብ ወልድን ከምንም (እምኀበ አልቦ) ፈጠረውና የእግዚአብሔር ልጅ አደረገው፡፡ አብም ወልድን ከፈጠረው በኋላ ሥልጣንን ሰጥቶት ዓለሙን ሁሉ እንዲፈጥር አደረገው፤›› ብሎ ሲናገር አብዛኞቹ የጉባኤው አባላት በጌታችን ላይ የተናገረውን የጽርፈት (የስድብ) ቃል ላለመስማት ጆሯቸውን ሸፈኑ ይባላል፡፡

በክርክሩ ጊዜ ‹‹ወልደ አብ ኢየሱስ ክርስቶስ መድኃኒት ነው፤ አዳኛችን ነው፡፡ አዳኝ መሆኑን ካመንን የባሕርይ አምላክነቱን ማመን አለብን፡፡ የሚያድን እግዚአብሔር ብቻ መሆኑን ቅዱሳት መጻሕፍት ይመሰክራሉ፡፡ በቅዱሳት መጻሕፍት ምስክርነት የወልድ አምላክነት ከሰው ልጆች የመዳን ምሥጢር ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ወልድ የባሕርይ አምላክ ካልሆነ ግን እኛም አልዳንም ማለት ነው፡፡ በእርሱ መዳናችንን ካመንን ግን ያዳነን እሱ አምላክ መሆኑን ማወቅና ማመን አለብን፡፡ ፍጡር ፍጡራንን ማዳን አይችልምና፤›› ብሎ አትናቴዎስ አርዮስን ሲጠይቀውና ሲከራከረው የሰሙት አብዛኞቹ የጉባኤው አባላት በደስታ ተዋጡ፡፡ አርዮስ ‹‹ወልድ በምድር ሕይወቱ ታላቅ ትሕትናንና ተጋድሎን በማሳየቱ በባሕርይ ሳይሆን በጸጋ የአምላክነትን ክብር ስላገኘ ስግደት ይገባዋል፤›› ይላል፡፡ አትናቴዎስም ‹‹ክርስቶስ ከባሕርይ አባቱ ከአብ ጋር አንድ ነው፡፡ ነገር ግን ወልድ ፍጡር ነውካልን ለእርሱ የአምልኮ ስግደት ማቅረብ አማልኮ ባዕድ ነዋ!›› ሲለው አርዮስ መልስ አላገኘም፡፡

ከአርዮሳውያን ጋር የከረረ ክርክር የተደረገው በሁለት ጉዳዮች ነበር፤ እነዚህም ፩ኛ አርዮስ ወልድን ‹‹ፍጡር ነው›› ለማለት ‹‹ሀሎ አመ ኢሀሎ ወልድወልድ ያልነበረበት ጊዜ ነበር›› ሲል ኦርቶዶክሳውያን ወልድን ዘለዓለማዊ ነው ለማለት ‹‹አልቦ አመ ኢሀሎ ወልድወልድ ያልኖረበት ጊዜ የለም›› ብለው የአርዮሳውያንን ክሕደት አጥላልተው አወገዙት፡፡ ፪ኛ አርዮስና ደጋፊዎቹ ‹‹ወልድ በባሕርዩ (በመለኮ) ከአብ ጋር አንድ አይደለም፤›› የሚሉትን ጉባኤው ካወገዘ በኋላ፣ ኦርቶዶክሳውያን ወልድን “Omo-ousios” (ዋሕደ ባሕርይ ምስለ አብ ወይም ዘዋሕድ ምስለ አብ በመለኮቱወልድ ከአብ ጋር በባሕርዩ በመለኮቱ አንድ ነው)›› አሉ፡፡ የአርዮስ ደጋፊዎች የነበሩትም የአርዮስን የክሕደት ትምህርት ያልተቀበሉ በማስመሰልና ኦርቶዶክሳውያን በመምሰል “Omoi-ousios” (የወልድ ባሕርይ ከአብ ባሕርይ ጋር ተመሳሳይ ነው) ብለው ሐሳብ አቀረቡ፡፡ የእነዚህንም ሐሳብ ጉባኤው ፈጽሞ አልተቀበለውም ነበር፡፡ እነዚህም መንፈቀ አርዮሳውያን (Semi-Arians) ተብለው ተወግዙ፡፡

“Omo-ousios” (ዋሕደ ባሕርይ ምስለ አብ በመለኮቱ ወይም ዘዋሕድ ምስለ አብ በመለኮቱ) የሚለውን ሐረግ አርዮሳውያንና መንፈቀ አርዮሳውያን አጥብቀው ተቃውመውት ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ የኮርዶቫው ኤጲስቆጶስ ኦስዮስና የእስክንድርያው ሊቀ ዲያቆን አትናቴዎስ ባቀረቡት ሐሳብ መሠረት “Omo-ousios” (ዋሕደ ባሕርይ ምስለ አብ በመለኮቱ ወይም ዘዋሕድ ምስለ አብ በመለኮቱ ወይም ዘዕሩይ ምስለ አብ በመለኮቱ) የሚለው ሐረግ ተጨምሮበት፣ የወልደ አብ ኢየሱስ ክርስቶስን አምላክነት የሚያረጋግጥ ፯ አናቅጽ ያሉት ቃለ ሃይማኖት (ጸሎተ ሃይማኖት) ተዘጋጅቶ ቀረበና የጉባኤው አባቶች ሁሉ ፈረሙበት፡፡ ከጸሎተ ሃይማኖት ፯ አንቀጾች መካከል የመጀመሪያው አንቀጽ የሚከተለው ነው፤

‹‹ሁሉን በያዘ፣ ሰማይንና ምድርን፣ የሚታየውንና የማይታየውን በፈጠረ በአንድ አምላክ በእግዚአብሔር አብ እናምናለን፡፡ ዓለም ሳይፈጠር ከእርሱ በተወለደ፣ የአብ አንድ ልጁ በሚሆን በአንድ ጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ እናምናለን፡፡ ከብርሃን የተገኘ ብርሃን፣ ከእውነተኛ አምላክ የተገኘ አምላክ፣ የተወለደ እንጂ ያልተፈጠረ፣ በመለኮቱ ከአብ ጋር አንድ የሚሆን፣ ሁሉ በእርሱ የሆነ (የተፈጠረ) በሰማይም  በምድርም፡፡ ስለ እኛ ስለ ሰዎች እኛን ለማዳን ከሰማይ የወረደ፤ ሥጋ የሆነ፡፡ ሰው ሆኖም ስለ እኛ የታመመ፡፡ በሦስተኛውም ቀን ከሙታን ተለይቶ የተነሣ፡፡ ወደ ሰማይ የዐረገ፡፡ በሕያዋንና በሙታን ይፈርድ ዘንድ ዳግመኛ የሚመጣ፡፡ በመንፈስ ቅዱስም እናምናለን፡፡››

በመጨረሻም ከዚህ በላይ እንደተገለጠው ጉባኤው የወልድን አምላክነትና በባሕርይ (በመለኮት) ከአብ ጋር አንድ መሆኑን በውል አረጋግጦና ወስኖ አርዮስንና መንፈቀ አርዮሳውያንን አውግዞ ከማኅበረ ክርስቲያን ለይቷቸዋል፡፡ አርዮስና የተወገዙት አርዮሳውያን ሁሉ በንጉሠ ነገሥቱ እንዲጋዙ ተደርገዋል፡፡

፪. በኢትዮጵያ ጸሎተ ሃይማኖት በተለይ የ‹‹Omoousios tw patri›› ትርጕም

‹‹Omoousios tw patri›› የሚለው የግሪኩ ሐረግ በግእዝ የተተረጐመው ‹‹ዘዕሩይ ምስለ አብ በመለኮቱ›› ተብሎ ሲሆን፣ በአማርኛው ነጠላ ትርጕም ግን ‹‹በመለኮቱ ከአብ ጋር የሚተካከል›› ተብሎ ነው የተተረጐመው፡፡ የግሪኩ ቃል የሚገልጠው ‹‹በመለኮቱ ከአብ ጋር አንድ የሚሆን›› ማለትን ነው፡፡ ‹‹የሚተካከል›› የሚለው ቃል ግን የግሪኩንም ሆነ የግእዙን ሐረግ አይወክልም፡፡ እንዳውም ‹‹መተካከል›› የሚለው ቃል መመሳሰልን ወይም ምንታዌን (ሁለትዮሽን) ነው እንጂ አንድነትን አይገልጥም፡፡ ይህ ደግሞ የመንፈቀ አርዮሳውያንን ሐሳብ ስለሚመስል የኢትዮጵያ ሊቃውንት የአማርኛውን ትርጕም እንደገና ሊያስቡበት ይገባል፡፡ በእርግጥ ‹‹ዐረየ›› ማለት ‹‹ተካከለ ማለት ነው፡፡ አለቃ ኪዳነ ወልድ እንደሚሉት በሌላ መንገድ ግን ‹‹ዐረየ›› የሚለው ግስ ‹አንድ ሆነ የሚል ትርጕም አለው፡፡ ለምሳሌ ‹‹ወምስለ ብሉይ ኢይዔሪ›› የሚለው ኃይለ ቃል ‹‹ከአሮጌው ጋር አንድ አይሆንም›› ተብሎ ይተረጐማል፡፡ እንደዚሁም በመዝሙረ ዳዊት ‹‹እስመ ተማከሩ ኅቡረ ወዐረዩ›› የሚለው ኃይለ ቃል ‹‹አንድ ሆነው በአንድነት ተማክረዋልና›› የሚል ትርጕም አለው፡፡

ስለዚህ ‹‹ዘዕሩይ ምስለ አብ በመለኮቱ›› የሚለው ሐረግ ‹‹በመለኮቱ ከአብ ጋር አንድ የሚሆን›› ተብሎ መተርጐም አለበት፡፡ ‹‹በመለኮቱ ከአብ ጋር የሚተካከል›› ከተባለ ግን ይህ መንፈቀ አርዮሳዊ አነጋገር ይሆናል፡፡ ምክንያቱም መንፈቀ አርዮሳውያን ‹‹ወልድ ከአብ ጋር በመለኮት ይመሳሰላል እንጂ አንድ አይደለም›ነው የሚሉት፡፡ ሃይማኖተ አበውን የተረጐሙ አባቶችም ‹‹ዐረየ›› ወይም ‹‹ዕሩይ›› የሚለውን ቃል ‹አንድ የሆነ› ብለው ነው የተረጐሙት፡፡ ለምሳሌ ‹‹ወውእቱ ዕሩይ ምስሌሁ በመለኮት›› የሚለውን ሲተረጕሙ ‹‹እርሱም በመለኮት ከአብ ጋር አንድ ነው›› ብለውታል፡፡ እንደዚሁም ‹‹ነአምን በሥላሴ ዕሩይ በመለኮት›ሲተረጐም ‹‹በመለኮት አንድ በሚሆኑ በሥላሴ እናምናለን›› ተብሎ ነው፡፡ በተመሳሳይ መልኩ ‹‹ወበከመ ወልድ ዕሩይ ምስለ አብ በመለኮቱ›› የሚለው ኃይለ ቃል ትርጕም ‹‹ወልድ በባሕርዩ ከአብ ጋር አንድ እንደ ሆነ›› ማለት ነው፡፡ እንደዚሁም የቅዳሴው የአንድምታ ትርጕም ‹‹ዘዕሩይ ምስለ አብ በመለኮቱ›› የሚለውን ኃይለ ቃል የተረጐሙት ሊቅ ‹‹ከአብ ጋር በመለኮቱ አንድ የሚሆን›› በማለት ነው፡፡

እንግዲህ ‹‹ዘዕሩይ ምስለ አብ በመለኮቱ›› የሚለው ኃይለ ቃል ‹‹ከአብ ጋር በመለኮቱ አንድ የሚሆን›› ተብሎ ከተተረጐመ ምንም የእምነት ጕድለት ወይም ስሕተት አይኖረውም፡፡ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስም ይህን ኃይለ ቃል ‹‹ዘዕሩይየሚተካከል›› ተብሎ እንዳይተረጐም ብለው ‹‹ዘዋሕድ ምስለ አብ በመለኮቱ›› በማለት አርመዉታል፡፡ ትርጕሙ ጥሩ ነው፤ ነገር ግን ‹‹ዘዕሩይ›› የሚለው ቃል የወጣበት ‹‹ዐረየ›› የሚለው ግስ ከላይ እንደተገለጸው ‹‹አንድ ሆነ›› የሚል ትርጕም ስላለው ‹‹ዘዕሩይ›› የሚለው ግእዙ ባይለወጥ ጥሩ ይመስለኛል፡፡ መስተካከል ያለበት ግእዙ ሳይሆን የአማርኛው ትርጕም ነው፡፡ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስም በዋናው ጸሎተ ሃይማኖት ላይ ‹‹ዘዕሩይ›› የሚለውን ቃል ሳያርሙ እንዳለ አስቀምጠውታል፡፡

ይቆየን

አርዮስ እና መንፈቀ አርዮሳውያን በቤተ ክርስቲያን ላይ ያደረሱት ችግር – ክፍል ሁለት

በቀሲስ ዶ/ር ምክረ ሥላሴ ገብረ አማኑኤል

ኅዳር ፲ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

ተፍጻሜተ ሰማዕት ቅዱስ ጴጥሮስ በሰማዕትነት ከሞተ በኋላ በ፫፻፲፪ ዓ.ም አርኬላዎስ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳስ (ፓትርያርክ) ሆኖ በምትኩ ተሾመ፡፡ በዚህ ጊዜ አርዮስ ከክሕደቱ የተጸጸተ መስሎ ወደ ፓትርያርክ አርኬላዎስ ቀረበ፡፡ የአርዮስ ደጋፊዎችም ፓትርያርኩ ከውግዘቱ እንዲፈታው በአማላጅነት በመቅረባቸው፣ አዲሱ ፓትርያርክ የቀድሞውን ፓትርያርክ የተፍጻሜተ ሰማዕት ጴጥሮስን ትእዛዝና አደራ በመዘንጋት አርዮስን ከውግዘቱ ፈታው፡፡ ይባስ ብሎም የቅስና ማዕረግ ሰጥቶ ሾመው፡፡ ሆኖም አርኬላዎስ አንድ ዓመት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ በሞት ተለየ፡፡ የሰማዕቱን የቅዱስ ጴጥሮስን ቃል ባለመጠበቁ የመቅሠፍት ሞት ነው የሞተው ይባላል፡፡

በአርኬላዎስም ምትክ ስመ ጥሩውና በዘመኑ ሁሉ ለቤተ ክርስቲያን እጅግ የተጋደለ አባት እለእስክንድሮስ (፫፻፲፪ – ፫፻፳፰ ዓ.ም) በካህናትና ምእመናን ተመርጦ ተሾመ፡፡ እለእስክንድሮስ ወዲያውኑ የአርዮስን የክሕደት ትምህርት በይፋ እየተቃወመ አርዮስን በጥብቅ አወገዘ፡፡ የአርዮስ ደጋፊዎች አርዮስን ከፓትርያርኩ ጋር ለማስማማት አጥብቀው ቢሞክሩም ፓትርያርክ እለእስክንድሮስ አልበገርም አለ፡፡ አርዮስ ተጸጽቶ፣ ስሕተቱን ለጌታ ለኢየሱስ ክርስቶስ ተናዝዞ ከተመለሰ ጌታ ምልክት ስለሚሰጠው ያንጊዜ እርሱ እንደሚቀበለው ነግሮ አሰናበታቸው፡፡ አርዮስ በበኩሉ በድፍረት የክሕደት ትምህርቱን ማሠራጨት ቀጠለ፡፡ ሕዝቡም ትምህርቱን በቀላሉ እንዲቀበለው የክሕደት ትምህርቱን በግጥምና በስድ ንባብ እያዘጋጀ ያሠራጭ ጀመር፡፡ ያም የግጥም መጣጥፍ ‹ታሊያ› ይባል ነበር፡፡ ትርጕሙም ማዕድ ማለት ነው፡፡ ሕዝብ ደግሞ ግጥም ማንበብ ስለሚወድና በግጥም መልክ ያነበበውን ስለማይዘነጋው የአርዮስን ትምህርት ለመቀበል ደርሶ ነበር፡፡

ሊቀ ጳጳሱ እለእስክንድሮስም ምእመናን ከአርዮስ የክሕደት ትምህርት እንዲጠበቁ እየዞረ በማስጠንቀቅ ያስተምር ጀመር፡፡ ፓትርያርኩም በ፫፻፲፰ ዓ.ም በእስክንድርያና በአካባቢዋ የሚገኙትን ጳጳሳትና ካህናት ሰብስቦ አርዮስንና ተከታዮቹን በጉባኤ አወገዛቸው፡፡ አርዮስ ግን ከስሕተቱ ባለመመለሱ ፓትርያርክ እለእስክንድሮስ በ፫፻፳፩ ዓ.ም አንድ መቶ የሚሆኑ የእስክንድርያንና የሊብያን ኤጲስቆጶሳት ሰብስቦ ጉባኤ በማድረግ የአርዮስን ክሕደት በዝርዝር አስረዳቸው፡፡ ሲኖዶሱም ጉዳዩን በሚገባ ከመረመረ በኋላ አርዮስን በአንድ ድምፅ አወገዘው፡፡ አርዮስም በበኩሉ እየዞረ ‹‹እለእስክንድሮስ ሰባልዮሳዊ ነውየሰባልዮስን የክሕደት ትምህርት ያስተምራል›› እያለ የሊቀ ጳጳሱን የእለእስክንድሮስን ስም ማጥፋት ጀመረ፡፡ በመሠረቱ ከሰባልዮስ ትምህርት ጋር የሚቀራረበው ‹‹ወልድ ፍጡር ነው›› (ሎቱ ስብሐት) የሚለው የአርዮስ ትምህርት ነው እንጂ ‹‹ወልድ የባሕርይ አምላክ ነውከአብም ጋር በባሕርይ አንድ ነው (ዘዋሕድ ምስለ አብ በመለኮቱ)›› የሚለው ትምህርት አይደለም፡፡

የአርዮስ ትምህርት በእስክንድርያና በመላዋ ግብጽ ብዙም ተቀባይነት ባለማግኘቱ ወደ መካከለኛው ምሥራቅ ወደ ሦርያና አንጾኪያ እየዞረ ቀድሞ ጓደኞቹ ለነበሩትና የእርሱን የክሕደት ትምህርት ለሚደግፉ ጳጳሳት ሁሉ ፓትርያርክ እለእስክንድሮስ ያለ አግባብ እንዳወገዘውና እንዳባረረው ከመንገሩም በላይ ‹‹እለእስክንድሮስ የሰባልዮስን ትምህርት ያስተምራል›› እያለ ስሙን ያጠፋ ጀመር፡፡ በዚያ የነበሩት የአርዮስ የትምህርት ቤት ጓደኞች ጳጳሳት ለምሳሌ የኒቆምዲያው ኤጲስቆጶስ አውሳብዮስና የቂሣርያው ኤጲስቆጶስ አውሳብዮስ የአርዮስን ሐሳብ ይደግፉ ስለነበር አርዮስ የክሕደት ትምህርቱን እየዞረ እንዲያስተምር ፈቀዱለት፡፡ ከዚህም በላይ ደፍረው ፓትርያርክ እለእስክንድሮስ አርዮስን እንዲቀበለው ጠየቁለት፡፡ ፓትርያርክ እለእስክንድሮስ ግን ይህንን ጥያቄ አልተቀበለውም ነበር፡፡ እንደውም እለእስክንድሮስ በበኩሉ የአርዮስን የክሕደት ትምህርት በመቃወምና በማውገዝ ብዙ ደብዳቤዎችን በመላዋ ግብጽና በመካከለኛው ምሥራቅ ለሚገኙ ሊቃነ ጳጳሳትና ኤጲስ ቆጶሳት ያስተላልፍ ጀመር፡፡

በአርዮስ ደጋፊ በኒቆምዲያ ኤጲስቆጶስ አውሳብዮስ አሳሳቢነትና ሰብሳቢነት በ፫፻፳፪ እና ፫፻፳፫ ዓ.ም በተከታታይ ሁለት ጉባኤያትን አድርገው የአርዮስ ትምህርት ትክክለኛ መሆኑን በማብራራትና ‹‹የአርዮስ ሃይማኖት ትክክል ስለሆነ መወገዝ አይገባውም›› በማለት የእለእስክንድሮስን ውግዘት በመሻር ለአርዮስ ፈረዱለት፡፡ አርዮስም ወደ እስክንድርያ ተመልሶ ያንኑ የክሕደት ትምህርቱን በስፋት ያስተምር ጀመር፡፡ በአርዮስ ክሕደት ምክንያት የተነሣው ውዝግብ በመላው የክርስትና አህጉር ሁሉ በተለይም በምሥራቁ የሮም ግዛት በመሠራጨቱ ቤተ ክርስቲያንና የሮም ግዛት በሙሉ እጅግ ታወኩ፡፡ ጳጳሳትና መምህራን እርስበርሳቸው ይነታረኩ ጀመር፡፡ በዚህም ሰላም ጠፍቶ በዚያው ወቅት የመላ የሮም ንጉሠ ነገሥት መንግ ሥት ብቸኛ ቄሣር የሆነውን ታላቁን ቈስጠንጢኖስ እጅግ አሳሰበው፡፡ ንጉሠ ነገሥት ቈስጠንጢኖስ በመላ ግዛቱ ሰላም እንዲሰፍን በመሻቱ ውዝግቡን በዲፕሎማሲያዊ መንገድ ለማብረድ መልእክተኞችን ደብዳቤ አስይዞ ወደየጳጳሳቱ ይልክ ጀመር፡፡ በደብዳቤውም የቃላት ጦርነት እንዲያቆሙና በሰላም እንዲኖሩ ይጠይቅ ነበር፡፡

ለዚህም መልእክት ጉዳይ ሽማግሌ የነበረውን በስፔን የኮርዶቫ ጳጳስ ኦስዮስን ወደ እስክንድርያ ደብዳቤ አስይዞ ላከው፡፡ ኦስዮስም በአንድ በኩል ከእለእስክንድሮስና ከግብጽ ኤጲስቆጶሳት ጋር፣ በሌላ በኩል ደግሞ ከአርዮስና ከእርሱ ደጋፊዎች ጋር ተወያይቶ በሁለቱ መካከል የነበረውን ልዩነት በሚገባ ከመረመረ በኋላ ወደ ንጉሠ ነገሥቱ ወደ ቈስጠንጢኖስ ተመልሶ ነገሩ ከባድ የሃይማኖት ጉዳይ ስለሆነ የመላው ሕዝበ ክርስቲያን ጳጳሳት የሚገኙበት ታላቅ ጉባኤ ተጠርቶ ውዝግቡ በጉባኤ ታይቶ ቢወሰን እንደሚሻል ለንጉሠ ነገሥቱ ምክር ሰጠ፡፡ ታላቁ ቈስጠንጢኖስም ምክሩን ተቀብሎ የመላው አብያተ ክርስቲያናት መሪዎች የሚሳተፉበት ዓለም አቀፋዊ ሲኖዶስ እንዲደረግ አዋጅ ነገረ፡፡ ጉባኤውም የቢታንያ አውራጃ ከተማ በሆነችው በኒቅያ እንዲሆን ተወሰነ፡፡ ለጉዞና ለኑሮ የሚያስፈልገው ወጪ ሁሉ ከመንግሥት ካዝና እንዲሆን ንጉሠ ነገሥቱ ትእዛዝ አስተላለፈ፡፡

ስለዚህም ቈስጠንጢኖስ በነገሠ በሃያ ዓመቱ በ፫፻፳፭ ዓ.ም በሮም ግዛት ውስጥ የነበሩት ሊቃነ ጳጳሳት፣ ኤጲስቆጶሳትና ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እንዲሰበሰቡ ጥሪ አስተላለፈ፡፡ እያንዳንዱ ኤጲስቆጶስ ሁለት ቀሳውስትንና ሦስት ምእመናንን (ሊቃውንትን) ይዞ እንዲመጣ ንጉሡ በፈቀደው መሠረት ብዙ ቀሳውስትና ምእመናን (ሊቃውንት) በጉባኤው ላይ ተገኝተው ነበር፡፡ ለጉባኤው የተሰበሰቡት አባቶችም ፫፻፲፰ ያህሉ ነበር፡፡ በጉባኤው የተሰበሰቡትን አባቶች ቍጥር የቤተ ክርስቲያን ጸሐፊዎች ከፊሎቹ ከፍ፣ ሌሎቹ ደግሞ ዝቅ አድርገው ይጽፋሉ:: ለምሳሌ የቂሣርያው አውሳብዮስ ፪፻፶ ነበሩ ሲል፣ ቴዎዶሬት ደግሞ ፪፻፸ ነበሩ ይላል፡፡ እንደዚሁም ሶቅራጥስ ፫፻፤ ሶዞሜን ደግሞ ፫፻፳ ነበሩ ይላሉ፡፡

በጉባኤው የተሰበሰቡት አባቶች በሕይወታቸው ንጽሕናና ቅድስና መሰል የሌላቸው፣ በሃይማኖታቸውም የሐዋርያትን ፈለግ የተከተሉ ነበሩ፡፡ ከዚህም ሁሉ ጋር በገቢረ ተአምራት ከፍ ያለ ዝና ያላቸው ነበሩ፡፡ በስብሰባውም ላይ ሃያ አርዮሳውያን ኤጲስቆጶሶች፣ የተወሰኑ አርጌንሳውያንና የፍልስፍና ምሁራን ተጠርተው መጥተው ነበር፡፡ የጉባኤው የክብር ፕሬዝዳንት ንጉሠ ነገሥቱ ታላቁ ቈስጠንጢኖስ ሲሆን፣ ጉባኤውን በሊቀ መንበርነት እንዲመሩ የተመረጡት ሦስት ሊቃነ ጳጳሳት ነበሩ፡፡ እነዚህም፡- የእስክንድርያው ሊቀ ጳጳስ አቡነ እለእስክንድሮስ፣ የአንጾኪያው ሊቀ ጳጳስ ኤዎስጣቴዎስ እና የኮርዶቫው (የእስፔኑ) ጳጳስ ኦስዮስ ነበሩ፡፡ ከጉባኤው ተካፋዮች መካከል እጅግ የታወቁ ምሁራን ነበሩ፡፡

ከእነዚህም ጥቂቶቹ እጅግ የተማረ፣ ንግግር ዐዋቂና ለኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ቀናተኛ የነበረው፣ የእስክንድርያ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ዲያቆን ሆኖ ለሊቀ ጳጳሱ ለእለእስክንድሮስ እንደ አፈ ጉባኤ የነበረው አትናቴዎስና ስመ ጥር የነበረው የቂሣርያው አውሳብዮስ ነበሩ፡፡ እንደዚሁም በዘመነ ስደት ጊዜ ለሃይማኖታቸው ብዙ ሥቃይ የተቀበሉ፣ ዓይናቸው የጠፋ፣ እጅ ወይም እግራቸው የተቆረጠ በቅድስናቸው የታወቁ አባቶችም ነበሩ፡፡ ከዚህም ሌላ በምንኵስና እና በብሕትውና ኑሯቸው እጅግ የታወቁ፣ የዛፍ ሥርና ቅጠል ብቻ በመብላት ይኖሩ የነበሩ፣ ተአምራትን በማድረግ በክርስቲያኖች ዘንድ እጅግ የተከበሩ አባቶች ነበሩ፡፡

ጉባኤው በአብዛኛው የተካሔደው በኒቅያ ከተማ በምትገኘው በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን ሲሆን፣ አንዳንድ ጊዜ ደግሞ እዚያው ኒቅያ በሚገኘው በንጉሠ ነገሥቱ ቤተ መንግሥት አዳራሽ ይካሔድ እንደነበር ይነገራል፡፡ ጉባኤውም በሦስት ቡድን የተከፈለ ነበር፤ ይኸውም የመጀመሪያው የኦርቶዶክሳውያን፣ ሁለተኛው የአርዮሳውያን፣ ሦስተኛው ደግሞ የመንፈቀ አርዮሳውያን ቡድን ሲሆን፣ በመጀመሪያው ቡድን የነበሩት ኦርቶዶክሳውያን መሪዎችም የእስክንድርያው ሊቀ ጳጳስ እለእስክንድሮስ፣ ሊቀ ዲያቆኑ አትናቴዎስ፣ የአንጾኪያው ሊቀ ጳጳስ ኤዎስጣቴዎስ፣ የኮርዶቫው (የእስፔኑ) ኤጲስቆጶስ ኦስዮስ፣ የአንኪራው (ዕንቆራው) ኤጲስቆጶስ ማርሴሎስ ወዘተ. ነበሩ፡፡

ከእነዚህም ሁሉ በክርክሩ ወቅት ጠንካራና ከባድ ክርክር ይከራከር የነበረውና፣ ለተቃዋሚዎቹ አፍ የሚያስይዝ ምላሽ ይሰጥ የነበረው የእስክንድርያው ሊቀ ዲያቆን አትናቴዎስ ነበር፡፡ በሁለተኛው ቡድን የነበሩትም አርዮስና የንጉሡ ወዳጅ የነበረው የኒቆምዲያው ኤጲስቆጶስ አውሳብዮስ፣ የኒቅያው ኤጲስቆጶስ ቴኦግኒስ፣ የኬልቄዶን ኤጲስቆጰስ ማሪስና የኤፌሶን ኤጲስቆጶስ ሜኖፋንቱስ ነበሩ፡፡ አርዮስ ግን ተከሳሽ ስለነበረ በየጊዜው በጉባኤው እየተጠራ መልስ ይሰጥ ነበር እንጂ የሲኖዶሱ ተካፋይ አልነበረም፡፡ ሦስተኛው ቡድን የመንፈቀ አርዮሳውያን (የመሀል ሰፋሪዎች) ቡድን ሲሆን፣ የእነርሱ ወኪልም የታወቀው የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ጸሐፊ የቂሣርያው ኤጲስቆጶስ አውሳብዮስ ነበር፡፡ ይህ ሰው መንፈቀ አርዮሳዊ ሆኖ ከቆየ በኋላ በመጨረሻ ወደ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ተመልሷል፡፡

ይቆየን

አርዮስ እና መንፈቀ አርዮሳውያን በቤተ ክርስቲያን ላይ ያደረሱት ችግር – ክፍል አንድ

በቀሲስ ዶ/ር ምክረ ሥላሴ ገብረ አማኑኤል

ኅዳር ፱ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

በመጀመሪያው አራት መቶ ዓመታት ውስጥ ቤተ ክርስቲያን በብዙ አቅጣጫ የተለያዩ ችግሮች ደርሰውባት እጅግ ስትሠቃይ ቆይታለች፡፡ በቤተ ክርስቲያን ላይ የደረሱት ችግሮችም ከሁለት አቅጣጫዎች የመጡ ነበሩ፤ አንደኛው ከቤተ ክርስቲያን ውጭ ሲሆን ሁለተኛው ከዚያው ከቤተ ክርስቲያን ውስጥ የተነሡ ችግሮች ነበሩ፡፡ በመጀመሪያው አብዛኛውን ጊዜ ችግር የተነሣው ከአሕዛብ ነገሥታት ሲሆን፣

፩ኛ/ የሮም መንግሥት ገዢዎችና በክፍላተ ሀገሩ የነበሩት የእነርሱ ወኪሎች እነሱ ያመልኩአቸው የነበሩትን ጣዖታት ክርስቲያኖች ስለማይቀበሉና ጨርሰውም ስለሚያወግዙ፤

፪ኛ/ አሕዛብ ያደርጉት እንደነበረው ክርስቲያኖች ለሮም ነገሥታት የአምልኮ ክብር ስለማይሰጡ፣ በቤተ ክርስቲያን ላይና በክርስቲያኖች ላይ በየጊዜው ስደት ታውጆ ክርስቲያኖች ሲሠቃዩ ኖረዋል፡፡

፫ኛ/ የጣዖታት ካህናትና የጣዖታት ምስል ሠራተኞች በክርስትና ሃይማኖት መስፋፋት ምክንያት የጣዖት አምልኮ እጅግ ስለቀነሰና በአንዳንድ ቦታዎችም አምልኮ ጣዖት ጨርሶ ስለቀረ ኑሮአቸው በመቃወሱ፣ ከአሕዛብ ነገሥታት ጋር በመወገን በክርስቲያኖች ላይ ልዩ ልዩ ችግሮች ይፈጥሩ ነበር፡፡

በቤተ ክርስቲያን ላይ ከውስጥ የተነሡ ችግሮችም እጅግ የበዙና የከፉም ነበሩ፡፡ ከመጀመሪያ ጀምሮ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ብዙ መለያየትና መከፋፈል ስለታየ አንዲት ቤተ ክርስቲያን ለብዙ ክፍሎች ትከፋፈል ይሆናል ተብሎ ተፈርቶ ነበር፡፡ በግብረ ሐዋርያት ላይ እንደተጠቀሰው ከአይሁድ ወገን ወደ ክርስትና በገቡትና ከአሕዛብ ወገን ወደ ክርስትና በገቡት ክርስቲያኖች መካከል የታዩት ብዙ ልዩነ ቶች ነበሩ፡፡ ይህ ችግር በ፶፩ ዓ.ም በተደረገው በሐዋርያት ጉባኤ በተሰጠው ውሳኔ መፍትሔ አግኝቶ በመጠኑም ቢሆን ችግሩ ተወግዶ ነበር፡፡ በኋላ ደግሞ በሁለተኛውና በሦስተኛው መቶ ዓመት ላይ ተነሥተው የነበሩት ዶኬቲኮች፣ ግኖስቲኮችና የሰባልዮስና የጳውሎስ ሳምሳጢ ተከታዮች የነበሩ መናፍቃን ተነሥተው በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ብዙ የከፋ ብጥብጥ ተነሥቶ ነበር፡፡

ይህም ችግር በየክፍላተ ሀገሩ በተጠሩ ሲኖዶሶች (ጉባኤዎች) የቤተ በክርስቲያን አንድነት ተጠብቆ ቆይቷል፡፡ እንደዚሁም በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ስለምሥጢረ ሥላሴ ዶግማ (ትምህርት) በቤተ ክርስቲያን መምህራን መካከል ብዙ ልዩነቶች ተፈጥረው ነበር፡፡ የእነጳውሎስ ሳምሳጢና የእነሰባልዮስ የኑፋቄ ትምህርቶች በቤተ ክርስቲያን አህጉራዊ ጉባኤያት (ሲኖዶሶች) ተወግዘው በዚህ ምክንያት የተነሣው ውዝግብ ጥቂት ረገብ ብሎ ነበር፡፡ ነገር ግን ከግማሽ ምእት ዓመት በኋላ በአርዮስ የምሥጢረ ሥላሴ ትምህርት ምክንያት ማለት አርዮስ ‹‹ወልድ ፍጡር ነው›› (ሎቱ ስብሐት) ብሎ በመነሣቱ ቤተ ክርስቲያን ለብዙ ዓመታት ስትታወክና ስትበጠበጥ ቆይታለች፡፡

፩. የአርዮስ የክሕደት (የኑፋቄ) ትምህርት

አርዮስ ከሦስተኛው ምእት ዓመት አጋማሽ በኋላ በ፪፻፷ ዓ.ም አካባቢ በሰሜን አፍሪካ በሊብያ ነው የተወለደው፡፡ ስሙ እንደሚያመለክተው የትውልድ ዘሩ (የዘር ሐረጉ) የሚዘዘው ከግሪክ ሲሆን፣ የተገኘውም ከክርስቲያን ቤተሰብ ነበር፡፡ በትውልድ ሀገሩ መሠረታዊ ትምህርቱን ከአጠናቀቀ በኋላ እስክንድርያ በሚገኘው ከፍተኛ መንፈሳዊ ትምህርት ቤት ገብቶ ከፍተኛ ትምህርት ተምሯል፡፡ አርዮስ በእስክንድርያ ከፍተኛ ትምህርት ቤት ትምህርቱን ካጠናቀቀ በኋላ ወደመካከለኛው ምሥራቅ ሔዶ በአንጾኪያ ከፍተኛ መንፈሳዊ ትምህርት ቤት ገብቶ ከፍተኛ የትርጓሜ መጻሕፍት ትምህርትና የነገረ መለኮት ትምህርት ተምሯል፡፡ መምህሩም የታወቀው ሉቅያኖስ ነበር፡፡ ከእስክንድርያ ትምህርት ቤት ይልቅ የአንጾኪያ ትምህርት ቤት ለአርዮስ የክህደት ትምህርት ቅርበት እንደነበረው ብዙ ሊቃውንት ይናገራሉ፡፡

አርዮስ አብዛኛውን የኑፋቄ ትምህርቱን ያገኘው ከሉቅያኖስና ከአንጾኪያ ትምህርት ቤት ነው፡፡ በአንጾኪያ የሚፈልገውን ትምህርት ከጨረሰ በኋላ ወደ እስክንድርያ ተመልሶ ኑሮውን በዚያው አደረገ፡፡ አርዮስ እጅግ ብልህና ዐዋቂ ሰው በመሆኑ ብዙ ሰዎች ያደንቁት ነበር፡፡ አንደበተ ርቱዕም ስለነበረ ተናግሮ ሕዝብን በቀላሉ ማሳመን እንደሚችል ይነገርለታል፡፡ በዚያ በነበረው ዕውቀትና ታላቅ የንግግር ችሎታ የእስክንድርያ ፓትርያርክ የነበረው ተፍጻሜተ ሰማዕት ቅዱስ ጴጥሮስ ዲቁና ሾመው፡፡ የእስክንድርያ ከፍተኛ ትምህርት ቤት ከከፍተኛ መንፈሳዊ ትምህርት ሌላ የግሪክ ፍልስፍናን በተለይም የፕላቶንን ፍልስፍና ያስተምሩ ስለነበር፣ አርዮስም ፍልስፍናን በተለይም ሐዲስ ፕላቶኒዝም (Neo-Platonism) የተባለውን ፍልስፍና በሚገባ ተምሯል፡፡

በዚህም የእስክንድርያውን ከፍተኛ ትምህርት ቤት ታላቅ መምህር የነበረውን የአርጌንስን (Origen) የተዘበራረቀ የምሥጢረ ሥላሴን ትምህርት ተከትሎ መጓዝ ጀመረ፡፡ አርጌንስ በምሥጢረ ሥላሴ ትምህርቱ አብን ከወልድ፣ ወልድን ደግሞ ከመንፈስ ቅዱስ በማዕረግና በዕድሜ ያበላልጥ ነበር፡፡ አርጌኒስ አብን፣ ወልድንና መንፈስ ቅዱስን በማበላለጥ አብ ከወልድ እንደሚበልጥ፣ መንፈስ ቅዱስ ደግሞ ከወልድ እንደሚያንስ ያስተምር ነበር፡፡ ስለዚህ የአርዮስ የክህደት ትምህርቱ ዋናው መሠረት አርጌኒስ እንደሆነ አያጠራጥርም፡፡ ምንም እንኳን አርጌኒስ ስለቅድስት ሥላሴ ቢያስተምርም፣ አርዮስ አጥብቆ የተናገረውና የኑፋቄ ትምህርቱን ያስተማረው ስለአብ እና ስለወልድ ነበር፡፡ በአጠቃላይ የአርዮስ የክሕደት ትምህርት የሚከተለው ነው፤

፩. አብ ብቻ ዘለዓለማዊ (ዘአልቦ ጥንት ወኢተፍጻሜት) ነው፡፡ ወልድ ግን ዘለዓለማዊ አይደለም፡፡ ነገር ግን እርሱ ያልነበረበት ጊዜ ነበር ለማለት ‹‹ሀሎ አመ ኢሀሎ›› (እርሱ ያልነበረበት ጊዜ ነበር) እያለ ያስተምር ጀመር፡፡ ስለዚህ አብ አባት ተብሎ የተጠራውና እንደ አባት የታወቀው ከዘመናት በኋላ እንጂ ከዘመናት በፊት አብ ተብሎ አይጠራም አለ፡፡ ይህንን ያለው ‹‹ወልድ ፍጡር ነው›› (ሎቱ ስብሐት) ብሎ ያልነበረበት ጊዜ ነበረ ለማለት ነበር፡፡

፪. የአርዮስ ዋናው የክሕደት ትምህርቱ ‹‹ወልድ ፍጡር ነው›› (ሎቱ ስብሐት) ማለትም ‹‹ወልድ ከመፈጠሩ በፊት አልነበረም፤›› የሚል ነው፡፡ ‹‹አብወልድን ከምንም ፈጠረና የእግዚአብሔር ልጅ እንዲሆን አደረገውለወልድ ጥበብ፣ ቃል የሚባሉ የኃይላት ስሞች አሉት›› እያለ ያስተምር ነበር፡፡ ለክሕደቱ መሠረት የሆነውና ሁልጊዜ ይጠቅሰው የነበረውም፡- ‹‹ትቤ ጥበብ ፈጠረኒ መቅድመ ሉ ተግባሩጥበብ ከፍጥረቱ ሁሉ አስቀድሞ እኔን ፈጠረኝ አለች፤›› ተብሎ በመጽሐፈ ምሳሌ ፰፥፳፪ ላይ የተጠቀሰው ኃይለ ቃል ነበር፡፡ በአርዮስ አስተሳሰብ ጥበብ የተባለ ወልድ ነው፤ ስለዚህ እግዚአብሔር አብ መጀመሪያ ወልድን ፈጠረ፡፡  ከዚያ በኋላ ወልድ ዓለምንና በውስጡ ያሉትን ሁሉ ፈጠረ ብሎ ያምን ነበር፡፡ ያለ ወልድ ምንም የተፈጠረ ፍጥረት የለም ብሎ ያስተምርም ነበር፡፡

፫. ከዚህም ሌላ አርዮስ ወልድን ከአብ ሲያሳንስ ‹‹ወልድ በባሕርዩ ከአብ ጋር አንድ አይደለም›› ይል ነበር፡፡ በሌላ በኩል ግን ወልድን ከሌሎች ከፍጡራን እጅግ ያስበልጠዋል፡፡ ወልድም በጸጋ የአብ ልጅ እንደሆነ ይናገራል፡፡ እንደዚሁም ወልድ በምድር ሕይወቱ ታላቅ ትሕትናንና ተጋድሎን በማሳየቱ በባሕርይ ሳይሆን በጸጋ የአምላክነትን ክብር እንዳገኘ አርዮስ በአጽንዖት ይናገር ነበር፡፡

፬. በአርዮስ አመለካከት ወልድ በባሕርዩ ፍጹም ስላልሆነ የአብን መለኮታዊ ባሕርይ ለማየትም ለማወቅም አይችልም ይል ነበር፡፡

፭. አርዮስ ስለ መንፈስ ቅዱስ ሲናገር ‹‹ወልድ ለአብ የመጀመሪያ ፍጥረቱ እንደሆነ፣ መንፈስ ቅዱስ ደግሞ ለወልድ የመጀመሪያ ፍጥረቱ ነው›› ይል ነበር፡፡

ይህን የአርዮስን ክሕደት የሰማው የእስክንድርያ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ (ፓትርያርክ) ተፍጻሜተ ሰማዕት ቅዱስ ጴጥሮስ አርዮስን አስጠርቶ የሚያስተምረው ትምህርት ሁሉ የተሳሳተ መሆኑን ገልጾለት ከስሕተቱ ተመልሶና ተጸጽቶ ከቅዱሳን አበው ሲተላለፍ በመጣው በኦርቶዶክስ እምነት እንዲጸና መከረው፡፡ አርዮስ ግን ከአባቱ ከተፍጻሜተ ሰማዕት ጴጥሮስ የተሰጠውን ምክር ወደ ጎን በመተው የክሕደት ትምህርቱን በሰፊው ማስተማር ቀጠለ፡፡ ይህንን የተመለከተ ያ ደግ አባት አርዮስን አውግዞ ከዲቁና ማዕረጉ ሻረው፡፡ የግብጽ ቤተ ክርስቲያን ትውፊት እንደሚለው፣ ተፍጻሜተ ሰማዕት ቅዱስ ጴጥሮስ አርዮስን ያወገዘው ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በራእይ ተገልጦለት በሰጠው ትእዛዝ መሠረት ነው፡፡

በአንድ ሌሊት በራእይ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ በአንድ ወጣት አምሳል እንደ ፀሓይ የሚያበራ ረጅም ነጭ ልብስ (ቀሚስ) ለብሶ ለቅዱስ ጴጥሮስ ይታየዋል፡፡ ልብሱ ለሁለት የተቀደደ ሆኖ ቢያየው ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ ደንግጦ ጌታን ‹‹መኑ ሰጠጣ ለልብስከልብስህን ማን ቀደደብህ?›› ብሎ ይጠይቀዋል፡፡ ጌታም ‹‹አርዮስ ልብሴን ቀደደብኝ›› ብሎ መለሰለት፡፡ ይኸውም በአባቶች ትርጕም ‹‹አርዮስ ከባሕርይ አባቴ ከአብ ለየኝ (አሳነሰኝ)›› ማለት ነው፡፡ ጌታም አርዮስን ከእንግዲህ ወዲያ ወደ ቤተ ክርስቲያን አንድነት እንዳይቀበለው አዝዞት ተሰወረ፡፡ ተፍጻሜተ ሰማዕት ጴጥሮስ ራእዩን ያየው በዲዮቅልጥያኖስ ስደት ጊዜ ተይዞ ለመገደል በእስር ቤት በነበረበት ወቅት ነበር፡፡ አርዮስም ቅዱስ ጴጥሮስ እንደሚገደል አውቆ ከውግዘቱ ሳይፈታው እንዳይሞት ከውግዘቱ እንዲፈታው አማላጆች ይልክበታል፡፡ ተፍጻሜተ ሰማዕት ቅዱስ ጴጥሮስ ግን አርዮስን ‹‹በሰማይና በምድር የተወገዘ ይሁን!›› በማለት ውግዘቱን አጸናበት፡፡ በዚያኑ ቀን ተማሪዎቹን አርኬላዎስን እና እለእስክንድሮስን አስጠርቶ ያየውን ራእይ በመግለጥ አርዮስን እንዳይቀበሉትና ከእርሱም ጋር ኅብረት እንዳይኖራቸው አዘዛቸው፡፡

ይቆየን