eresha be 3

የበኬ ደብረ ምሕረት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን የልማት ሥራ ተጎበኘ

ታኅሣሥ 1 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

 

eresha be 3በማኅበረ ቅዱሳን የአዲስ አበባ ማዕከል ሥራ አሥፈጻሚ አባላትን ያቀፈ የልዑካን ቡድን በበኬ ደብረ ምሕረት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን እየተከናወነ የሚገኘውን የልማት ሥራ ለመመልከትና ከደብሩ አስተዳደር አካላት ጋር ለመወያየት ኅዳር 23 ቀን 2005 ዓ.ም. ጉብኝት አካሄደ፡፡

 

የአዲስ አበባ ማእከል ከበኬ ደብረ ምሕረት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን አስተዳደርና ሰበካ ጉባኤ ጋር ባደረገው የውል ሥምምነትeresha be 2 መሠረት በባለሙያ አስጠንቶ ዘመናዊ የግብርና ኤክስቴንሽን መርሐ ግብሮች ተግባራዊ ለማድረግ ጥረት ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ በተያዘው እቅድ መሠረት እሰካሁን ከተከናወኑት ውስጥ ደግሞ የቤተ ክርስቲያኑ ይዞታ በሆነው 3 ሄክታር መሬት ላይ የተዘራው የጤፍ እርሻ የሚገኝበትን መቃኘት የመጀመሪያው የጉብኝቱ አካል ነበር፡፡

 

የጤፉ እርሻ ለዓይን ይማርካል፡፡ ከ250 አስከ 300 ካሬ ሜትር የሚሆነው ከሌላው ማሳ ለየት ባለ ሁኔታ በቁመትም፤ ሆነ በያዘው የፍሬ መጠን ከፍተኛነት ይለያል፡፡ ለአጨዳ የደረሰ በሚመስል መልኩ ወደ ቢጫነት አዘንብሏል፡፡ ቀሪውም ባማረ ሁኔታ ጎልቶ ይታያል፡፡ ከፍተኛ ክትትል እንደተደረገበትም ያመለክታል፡፡

 

የቤተ ክርስቲያኑ አስተዳዳሪ የሆኑት አባ ገብረ አማኑኤል ቦታው ጠፍ የነበረና የከብቶች መዋያ ሆኖ መቆየቱንና ይህንንም ችግር ለመቅረፍ ከማኅበረ ቅዱሳን አዲስ አበባ ማዕከል ጋር በተደረገው ስምምነት መሠረት በባለሙያ ተጠንቶና ታርሶ ፍሬ ለማየት እንደበቁ የገለጹ ሲሆን ወደፊትም ተደጋግፎ የተሻለ ሥራ ለመሥራት እንደተዘጋጁ በጉብኝቱ ላይ ተናግረዋል፡፡

 

“በእርሻ ሥራው ላይ የደብሩ ካህናት የንስሐ ልጆቻቸውን በማስተባበር፤ ለዘር የሚሆን ጤፍ በማቅረብ፤ በጉልጓሎና ዘር በሚዘራበት ውቅት ቤተሰቦቻቸውን ጭምር በማሰማራት፤ ቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ በመማር ላይ የሚገኙ ከ200 በላይ የአብነት ተማሪዎች፤ የደብሩ አስተዳደር፤ ካህናትና ዲያቆናት ተሳትፈውበታል፡፡ ምርቱም በመማር ላይ ለሚገኙት የአብነት ተማሪዎች የምግብ ፍጆታነት ይውላል” በማለት የገለጹት ደግሞ የቀድሞው የቤተ ክርስቲያኗ ሰበካ ጉባኤ ምክትል ሰብሳቢ የሆኑት አቶ ከፍያለው አየለ ናቸው፡፡

 

eresha be“የግብርና ኤክስቴንሽን መርሐ ግብሮችን ለመጠቀም ጥረት አድርገናል፡፡ ለማስተማር የፈለግነው የአካባቢው አርሶ አደሮችና ምእመናን ከቤተ ክርስቲያን በጎ ተሞክሮዎችን እንዲወስዱ ለማድረግ ነው፡፡ በበሬ ብቻ ሳይሆን በትራክተር እንዲታረስም አድርገናል፡፡ ከ3 ሄክታር መሬቱ ላይ ከ250 እሰከ 300 ካሬ ሜትሩ ለሙከራ ምርጥ ዘር ተጠቅመናል፡፡ የትኛው የተሻለ እንደሆነ ለሁሉም ለማሳየት የቻልንበት ነው፡፡ ገና ሳይታጨድ ልዩነቱም ጎልቶ ይታያል፡፡ በሚቀጥለው አመትም ጤፍ በመሥመር መዝራትን ተግባራዊ የምናደርግበት ሁኔታ እናመቻቻለን፡፡ ይህንን የምናደርገው ምእመናን የቤተ ክርስቲያናችንን ተሞክሮ ተመልክተው እነሱም እንዲጠቀሙበት ለማስተማር ነው፡፡” በማለት ወይዘሪት መቅደስ አለሙ በአዲስ አበባ ማእከል የማኅበራዊ አገልግሎትና ልማት ክፍል ሰብሳቢ በጉብኝቱ ላይ ገልጸዋል፡፡

 

በቀጣይነት የተካሄደው አብነት ትምህርት ቤቱ የሚገኝበት ሁኔታ ለመቃኘት የተደረገ ጉብኝት ነው፡፡ የአብነት ትምህርት ቤቱ በ3 መምህራን ከ200 በላይ ተማሪዎችን በማቀፍ የአቋቋም፤ የቅኔ፤ እንዲሁም የቅዳሴ ትምህርቶች የሚሰጥበት ተቋም ነው፡፡

 

በሁለት አዳራሾች ውስጥ መኝታቸውን ያደረጉት የአብነት ተማሪዎቹ የመኝታቸው ጉዳይ እጅግ አሳሳቢ ነው፤ አልጋቸው በርብራብ እንጨትeresha be 4 የተዘጋጁ ናቸው፤ የሳር ፍራሽና ካርቱን አንጥፈውበታል፡፡ አንዱን ከአንዱ ለመለየት በማዳበሪያ ተከፋፍሏል፤ በአንዱ አዳራሽ ውስጥ አዳራቸውን የሚያደርጉት ተማሪዎች ብዛት ከአንድ መቶ ይበልጣል፡፡ አዳራሹ ውስጥ እሳት ቢነሣ ወይም በሽታ ቢገባ የሚተርፍ ያለ አይመስልም፡፡ አንድ የማብሰያ ክፍል ሲኖር ሁሉንም ማስተናገድ ስለማይችል የተወሰኑት ተማሪዎች ውጪ ሜዳው ላይ ምግባቸውን ለማብሰል ይገደዳሉ፡፡

 

የቤተ ክተርስቲያኑ አስተዳደር ጉባኤ ያለውን ችግር በመረዳት ለሰንዳፋ በኬ የማኅበረ ቅዱሳን ማእከል፤ በቅደም ተከተልም ለአዲስ አበባና ለዋናው ማእከል የችግሩ አሳሳቢነት በማሳወቅ ጥናት ተደርጓል፡፡ በጥናቱ መሠረት የአብነት ትምህርት ቤቱን ለማደራጀትና ለማጠናከር ፤ ተማሪዎቹም ተምረው የነገዎቹ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እንዲሆኑ ለማስልቻል ጥረት በመደረግ ላይ  ይገኛል፡፡ በማኅበረ ቅዱሳን የአዲስ አበባ ማእከል ከፍተኛ በጀት በመመደብ የአብነት ትምህርት ቤቱን ዘመናዊ ሕንፃ ለመገንባት ዝግጅት በማድረግ ላይ እንደሚገኝና ግንባታውንም በዚህ ዓመት ይጀመራል ተብሎ እንደሚጠበቅ በጉብኝቱ ላይ ተገልጧል፡፡

 

በመጨረሻም በጋራ ውይይት የተካሄደ ሲሆን በቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ሥራዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ የሁሉም ድጋፍ እንደሚያስፈልግ የቤተ ክርስቲያኑ አስተዳዳሪ አባ ገብረ አማኑኤል ጥሪያቸውን ያስተላለፉ ሲሆን በልማት ሥራው ላይ ለተሣተፉ ሁሉ ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡ በጉብኝቱ ላይ የሰንዳፋ ወረዳ ቤተ ክህነት ሓላፊዎች፤ የደብሩ አስተዳደር፤ ካህናትና ዲያቆናት፤ የደብሩ የሰበካ ጉባኤ አባላት፤ የማኅበረ ቅዱሳን የሰንዳፋ ማእከል ሓላፊዎችና አባላት፤ ጥሪ የተደረገላቸው የአጥቢያው ምእመናን ተገኝተዋል፡፡

 

በኬ ደብረ ምሕረት ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን በዳግማዊ ዐፄ ምኒልክ ዘመነ መንግሥት በ1860ዎቹ ውስጥ እንደ ተተከለ ይነገራል፡፡

mkmesfin1

የማዕረግ ተመራቂው የወርቅ ሜዳልያውን ለማኅበሩ አበረከተ

29/03/2005ዓ.ም

በእንዳለ ደምስስ

ደብረ ዘይት በሚገኘው በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ እንስሳት ህክምናና ግብርና ኮሌጅ በ2004 ዓ.ም. የተመረቀው ዶክተር መስፍን ማሞ በአጠቃላይ ውጤት (GPA) 3.98  እጅግ በጣም ከፍተኛ ማዕረግ በማምጣት ተመርቋል፡፡ ኮሌጁም ላስመዘገበው ውጤት Outstanding Student Of The Year 2012 College Of Veternary & Agriculture በማለት ኮሌጁ በበላይነት ላጠናቀቁ ተማሪዎች የሚሰጠውን የወርቅ ሜዳልያ ሽልማት አበርክቶለታል፡፡

mkmesfin1

ዶክተር መስፍን ማሞ ይህንን ሽልማት በመያዝ ወደ ማኅበረ ቅዱሳን ዋናው ማዕከል በመምጣት “በትምህርቴ ባስመዘገብኩት ውጤት ያገኘሁት ሽልማት ነው፡፡ ለኔ አይገባኝም፡፡” በማለት ለማኅበሩ እንደሚሰጥ አሳወቀ፡፡

 

በርክክቡ ላይ ከኮሌጁ የተሸለመውን  የወርቅ ሜዳልያ ለማኅበረ ቅዱሳን  ለምን መሥጠት እንደፈለገ ዶክተር መስፍን ማሞ ሲገልጽ “ማኅበሩ በቤተ ክርስቲያናችን ዙሪያ በሀገር ውስጥም ሆነ በመላው ዓለም ከፍተኛ አገልግሎት እያበረከተ ይገኛል፡፡ ቤተ ክርስቲያንን በማስተዋወቅና ምዕመናንን በማስተማር እያበረከተ ላለው ጥረት ከፍተኛ አክብሮት አለኝ፡፡ በግቢ ጉባኤ አማካይነት በሥነ ምግባር የታነጸና የዓላማ ሠው እንድሆን ማኅበሩ ከፍተኛ እገዛ አድርጎልኛልና ያለኝን ታላቅ አክብሮት ለመግለጽ ስል ይህንን ከኮሌጁ የተሸለምኩትን የወርቅ ሜዳልያ ሰጥቻለሁ” ብሏል፡፡

mkmesfin2የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጸሐፊ ዲያቆን ሙሉጌታ ኃይለ ማርያም የወርቅ ሜዳልያውን በተረከቡበት ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት  “የማኅበረ ቅዱሳን አባላት በግቢ ጉባኤያት ቆይታቸው በትምህርታቸው ከፍተኛ ውጤት በማስመዝገብ የተሸለሙትን ሜዳልያ ለማኅበሩ ሲያበረክቱ ይህ ለሁለተኛ ጊዜ ነው፡፡

 

ተማሪዎች የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት ከመደበኛው ትምህርታቸው ውጪ ጊዜያቸውን በፕሮግራምና  በአግባቡ መጠቀም ከቻሉ ለውጤት መብቃት እንደሚችሉ መልዕክት የሚያስተላልፍ ነው፡፡ ሽልማቱ ለማኅበራችን እንዲሁም ለቤተ ክርስቲናችን ታላቅ ኩራት ነው፡፡” በማለት የገለጹ ሲሆን ዶክተር መስፍን ማሞ ላደረጉት አርአያነት ያለው ተግባር ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

 

ከዚህ ቀደም ከጅማ ጤና ሳይንስ ኮሌጅ በከፍተኛ ማዕረግ የተመረቁት ዲያቆን ዶክተር እንግዳ አበበ የተሸለሙትን የወርቅ ሜዳልያ ለማኅበረ ቅዱሳን በሥጦታ እንዳበረከቱ ይታወቃል፡፡

nebabe 2 1

የንባብ ባሕልን ለማሳደግ ውይይት ተካሄደ

ኅዳር 26 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ


የንባብ ባሕልን በማሳደግ በመረጃና በእውቀት የበለጸገ ማኅበረሰብ እንፍጠር በሚል ርዕስ የማኅበረ ቅዱሳን የጥናትና ምርምር ማእከልnebabe 2 1 ያዘጋጀው የውይይት መድረክ  ኅዳር 22 ቀን 2005 ዓ.ም. ከቀኑ 8፡00 ስዓት ላይ በማኅበሩ ሕንፃ ላይ ተካሄደ፡፡

 

ቀሲስ ዶ/ር ሰሙ ምትኩ የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ በመርሐ ግብሩ ላይ ለተገኙት እንግዶች የእንኳን ደህና መጣችሁ መልእክት ያስተላለፉ ሲሆን የውይይት መድረኩ የተዘጋጀበትን ዋነኛ ምክንያት ሲገልጹም “በሀገራችን ብሎም በቤተ ክርስቲያናችን በጣም በአሳሳቢ ሁኔታ እየቀነሰ የመጣውን የንባብ ባሕል ለማሳደግ እንዲቻል የተዘጋጀ የውይይት መድረክ ነው፡፡ የማያነብ ትውልድ አዲስ ነገር መፍጠር አይችልም፤ አዲስ ነገርንም ለመቀበል ያስቸግረዋል፡፡ የንባብ ባሕላችን ምን ላይ እንደሚገኝ፤ ያጋጠሙ ችግሮችና ሊወሰዱ የሚገባቸው መፍትሔዎች ላይ ለመወያትና እንዲሁም ቤተ ክርስቲያን ትውልዱን በእውቀትና በመረጃ ከማነፅና ከመቅረፅ አንጻር ሊኖራት የሚገባት ሚና ምን መሆን እንዳለበት ለማመላከት ነው፡፡” ብለዋል፡፡

 

nebabe 3የውይይት መድረኩ በአቶ ወንድወሰን አዳነ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የኢትዮጵያ ቋንቋዎች ሥነ ጽሑፍ ትምህርት ክፍል መምህር የተመራ ሲሆን ዲያቆን ያረጋል አበጋዝ ለውይይት መድረኩ መነሻ የሚሆን ጥናታዊ ጽሑፋቸውን አቅርበዋል፡፡ ባቀረቡት ጽሑፍም “ሥነ ፍጥረት የሚነበብ መጽሐፍ ነው፡፡ መጽሐፍ እግዚአብሔር በመጀመሪያ ለፍጥረቱ የሰጠው ትልቁ ሥጦታ  ነው፡፡” በማለት የጥናት ጽሑፋቸውን በመጀመር በመጽሐፍ ቅዱስ ስለ መጻሕፍት የተነገሩትን ጠቅሰዋል፡፡ ከእነዚህም መካከል” በእግዚአብሔር ቃል ሰማዮች ፀኑ፤ ሠራዊታቸውም ሁሉ በአፉ እስትንፋስ የባሕርን ውኃ እንደ ረዋት የሚሰበስብ ቀላዮችንም በመዝገቦች የሚያኖራቸው” መዝ.86፤6 “በእግዚአብሔር መጽሐፍ ፈልጉ አንብቡም አፌ አዟልና” (ኢሳይያስ 34፤16) በማለት ጠቅሰዋል፡፡ በተጨማሪም ከቅዱሳን አበው መካከል “ቅዱሳት መጻሕፍትን አለማወቅ የስህተት ሁሉ ምንጭ ነው” በማለት ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ከተናገረው በመነሣት የቅዱሳት መጻሕፍት ጠቀሜታን  አብራርተዋል፡፡

 

መጻሕፍትን የማንበብ ፋይዳን አስመልክቶም ተጠቃሽ ናቸው ያሏቸውን ነጥቦች አንሥተዋል፡፡ ከእነዚህም መካከል፤ መጻሕፍት በዘመናት ሂደት የተከማቹ የሰው ልጆች የእውቀት መዛግብት የሚተላለፍባቸው መንገዶች መሆናቸው፤ መጻሕፍት ጓደኛ ስለመሆናቸው፤ መጻሕፍት የመንፈስ ምግቦች መሆናቸው፤ መጻሕፍት አንድን ርዕሰ ጉዳይ ወጥና ምሉዕ በሆነ ሁኔታ ለመዳሰስ ያስችላሉ፤ መጻሕፍት ተጠቃሽ /Quatable/ ናቸው፤ መጻሕፍት በተሳሳተ መንገድ መጥቀስም መጠቀስም ባያስቀሩም ስህተቶችን ይቀንሳሉ፤ መጻሕፍት ትውልድን ይሻገራሉ በማለት የመጻሕፍትን ፋይዳ በዝርዝር ዳስሰዋል፡፡

 

ዲያቆን ያረጋል አበጋዝ የንባብ ልምድ በኢትዮጵያ አስመልክቶ ባቀረቡት ትንተናም በዚህ ርዕሰ ጉዳይ ላይ ጥናቶች በጥልቀት ያለመሠራታቸውና አንድ ጥናት አቶ አለም እሸቱ የተባሉ ተመራማሪ  ሙከራ ማድረጋቸውን ገልጸዋል፡፡ በጥናታቸውም መሠረት በ220 ሰዎች ላይ ለናሙና ያህል በቀረበ መጠይቅ ለምን መጻሕፍትን እንደማያነቡ በሰጡት ምላሽ “ላይኔ ስለምፈራ አላነብም፤ ሳነብ አይገባኝም፤ ምክንያቱን አላውቅም፤ የአውሮፓ እግር ኳስ እያለ እንዴት አነባለሁ፤ ትላልቅ መጻሕፍትን ሳይ ተስፋ ያስቆርጡኛል፤ ከቤተሰብ አልለመድኩም፤ ሴት ልጅ ቤት ውሰጥ ቁጭ ብላ ቤተሰብን ማገዝ እንጂ ለማንበብ አይፈቀድላትም ፤. . . የሚሉ ምላሾችን መስጠታቸው ንባብ በኢትዮጵያ ውስጥ አለማደጉን የሚያመላክቱ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡

 

በጥናታቸው ማጠቃለያም የንባብ ባሕልን ለማሳደግ መፍትሔ ይሆናሉ ያሏቸውንም ጠቁመዋል፡፡ የንባብ ፍላጎት እንዲኖር ማድረግ፤ ከሕፃንነት ጀምሮ የማንበብ ፍቅርና ልምድ እንዲኖር ማድረግ፤ የመጻሕፍት ስብስብና ክምችት መፍጠር እንደ መፍትሔ ካቀረቧቸው ውስጥ ይጠቀሳሉ፡፡

 

nebabe 2 2ጥናቱ ከቀረበ በኋላም በንባብ ባሕል ላይ ያተኮረ ውይይት የተካሄደ ሲሆን ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ የዩኒቨርስቲ ምሁራንና ተማሪዎች እንዲሁም ተሳታፊዎች አስተያየቶቻቸውንና የመፍትሔ አሳቦቻቸውን አቅርበዋል፡፡ በአብዛኛው ከተጠቀሱት ውስጥም የንባብ ባሕላችንን ለማሳደግ በዋነኛነት ቤተሰብና ትምህርት ቤቶች ከፍተኛ ሓላፊነት እንዳለባቸው ፤ ልጆች ከሕፃንነት ጀምሮ ንባብን ባሕል አድርገው እንዲያድጉ ከፍተኛ ሥራ መሠራት እንደሚገባው አመላክተዋል፡፡

 

በመጨረሻም ማኅበረ ቅዱሳን አንባቢ ትውልድን ለመፍጥር በሚያደርገው አገልግሎት ውስጥ መጻሕፍትን የማሰባሰብ፤ ቤተ መጻሕፍቱን በዘመናዊ መልክ የማደራጀት ሥራ በመሥራት ላይ እንደሚገኝና  በአሁኑ ወቅት ቤተ መጻሕፍቱ ከሁለት ሺህ የማይበልጡ መጻሕፍትን ብቻ አሰባስቦ አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን፤ በዐራት ዓመታት ውስጥም የመጻሕፍቱን ቁጥር ሃምሳ ሺህ ለማድረስ መታቀዱን የጥናትና ምርምር ማእከሉ ዋና ዳይሬክተር ዲያቆን ዮሐንስ አድገ የገለጹ ሲሆን ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ ምሁራንና ምእመናን አንባቢ ትውልድን ለመፍጠር በሚደረገው ጥረት ውስጥ እገዛ እንዲያደርጉ ጥሪያቸውን አቅርበዋል፡፡

 

በውይይቱ ላይ ጥሪ የተደረገላቸው ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ የዩኒቨርሲቲ ምሁራንና ተመራማሪዎች፤ እንዲሁም ተማሪዎችና ምእመናን ተገኝተዋል፡፡

የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን ተልዕኮ ለማሳካት የገዳማት ድርሻ!!

  • የወርቃማው ዘመን ወርቃማ ደራሲ የአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ የገድል መጽሐፍ  ይመረቃል

 

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ማኅበረ ቅዱሳን ጥንታውያን ገዳማት እና የአብነት ትምህርት ቤቶች ለማጠናከር ላለፉት 10 ዓመታት ዘላቂ የልማት ፕሮጀክቶችን በመቅረጽ ከምዕመናን በተገኘ የገንዘብ ድጋፍ ተግባራዊ ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ በዚህም አበረታች ውጤት ተመዝግቧል፡፡

 

ማኅበሩ ይህንን አገልግሎት አጠናክሮ ለመቀጠል ከ50 ጥንታውያን ገዳማት የተውጣጡ አበምኔቶች በተገኙበት “የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን ተልዕኮ ለማሳካት ገዳማት ያላቸው ድርሻ ”  በሚል መሪ ቃል ቅዳሜ ታኅሣሥ 6 ቀን 2005 ዓ.ም ከቀኑ 7፡00 ሰዓት ጀምሮ በኢትዮጵያ ስብሰባ ማዕከል በተቀናጀ ልማት ለውጥ ማምጣት እንደሚቻል የሚያሳይ መርሐ ግብር ተዘጋጅቷል፡፡

 

እርስዎም በዕለቱ ተገኝተው የመርሐ ግብሩ ተሳታፊ በመሆን የአባቶችን ቡራኬ በመቀበል ድርሻዎትን ይወጡ ዘንድ በአክብሮት ተጋብዘዋል፡፡

ረድኤተ እግዚአብሔር አይለየን

አድራሻ ፡- ስድስት ኪሎ ከምስካየ ኅዙናን መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን ከፍ ብሎ በኢትዮጵያ ስብሰባ ማዕከል
አዘጋጅ ፡-የማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል

dsc03541

የአሰቦት ገዳም የመንገድ ችግር በመቀረፍ ላይ ነው

ኅዳር 20 ቀን 2005 ዓ.ም.
በእንዳለ ደምስስ

•    በሁለት በጎ አድራጊ ወጣቶች የ6 ኪሎ ሜትር የተራራው አስቸጋሪ መንገድ ተሠራ
•    የ12 ኪሎ ሜትሩ መንገድ በመሠራት ላይ ነው

dsc03541የአሰቦት ደብረ ወገግ ቅድሥት ሥላሴና አቡነ ሳሙኤል ገዳም 6 ኪሎ ሜትር የተራራው መውጫ መንገድ በሁለት በጎ አድራጊ ወጣቶች ሙሉ ወጪውን በመሸፈን የጥርጊያ መንገዱን ሥራ ከመስከረም 7 ቀን 2005 ዓ.ም. ጀምሮ  በ17 ቀናት ውስጥ በመሥራት ተጠናቀቀ፡፡

የገዳሙ አበምኔት አባ ተክለ ማርያም ተክለ ፃድቅ ስለ መንገድ ሥራው ሲገልጹ “እግዚአብሔር አነሣሥቷቸው ይህ ቅዱስ ገዳም ያለበትን የመንገድ ችግር ተገንዝበው ሙሉ ወጪውን በመሸፈንና መንገዱ ተሠርቶ እስኪጠናቀቅ ድረስ እዚሁ ከእኛው ጋር በመሆን ሥራውን እየተቆጣጠሩ በአጭር ጊዜ ውስጥ ማጠናቀቅ ተችሏል፡፡ የመንገዱ መሠራት ገዳሙን ከእሳት ቃጠሎ፤ በተለይም የደን ጭፍጨፋ ከሚያካሂዱ አካላትና ከተለያዩ አደጋዎች ይታደገዋል፡፡ ምእመናንም ከዚህ ቅዱስ ሥፍራ በመገኘት በረከት እንዲቀበሉ ያስችላቸዋል፡፡ ለኛ ለገዳማውያንም መውጣት መውረዱን ያቀልልናል፡፡ ሁለቱ ወጣቶች ያከናወኑት በጎ ተግባር ሌሎችም አርአያነታቸውን ሊከተሉ ይገባል  ” ብለዋል፡፡

 

ቴዎድሮስ ሰሎሞን ይባላል፡፡ የ”ዴታና ቢዝነስ ሓላፊነቱ የተወሰነ ግል ማኅበር” ባለቤት ነው፡፡ የ6 ኪሎ ሜትር የተራራውን ጥርጊያ መንገድ ከጓደኛው ጋር በመሆን  ሙሉ ወጪውን በመሸፈን ለመሥራት በቅቷል፡፡ ምን እንዳነሣሣው ጠይቀነው ሲመልስ “አሰቦት ገዳም ላለፉት 10 ዓመታት በዓመታዊ ንግሥ በዓል ላይ በረከት ለማግኘት ተመላልሻለሁ፡፡ ዋነኛ ችግር ነው ብዬ የተመለከትኩትም ምእመናን ተራራውን ለመውጣት የሚያደርጉትን አድካሚ ጉዞ ነበር፡፡ አረጋውያን መውጣት ተስኗቸው በየመንገዱ እያረፉ ሲጨነቁና ሲጠበቡ እመለከታለሁ፡፡ ይህንን መንገድ መች ነው የምሠራው እያልኩ ሳስብ ቆይቻለሁ፡፡ አሰበ ተፈሪ የሚገኙ ወንድሞችን አማክሬያቸው ለኦሮሚያ ግብርና ጉዳዩን በማሳወቅና መንገዱን ለመቀየስ በሚደረገው ጥረት ውስጥ የሚወገዱ ዛፎችን ጉዳይ በመነጋገርና ፈቃድ በመውስድ የጥርጊያ መንገዱን ሥራ ከጓደኛዬ ጋር ተመካክረን የምሠራበትን ዶዘር ቦታው ድረስ በመውሰድ እግዚአብሔር የፈቀደልንን ያህል አባቶች በጸሎት እየተራዱን መንገዱን በማስፋትና በመጥረግ ለመኪናም ሆነ ለሰው በቀላሉ መውጣት እንዲያስችል ተደርጓል፡፡” ብሏል፡፡

“ከዚህ በፊት ወደ ገዳሙ ሄጄ አላውቅም፡፡ ጓደኛዬ  ወደዚህ ገዳም ይመላለስ ስለነበር የገዳሙን ችግር ይነግረኝ ነበር፡፡ አብረን ለመሥራት ተነጋግረን የራሴን ግሬደር በማምጣት በመቀየስና ተለዋጭ መንገድ በማዘጋጀት መንገዱን አስተካክለን ለገዳሙ አስረክበናል፡፡ ከዚህ በረከት ልሳተፍ በመቻሌ ተደስቻለሁ” በማለት የገለጸው ደግሞ የ”ዳክ የኮንስትራክሽን ማሽነሪዎች ኪራይ አገልግሎት” ድርጅት ባለቤት ወጣት ክብሮም ተክሌ ነው፡፡

dsc03547ሥራውን ለመሥራት በገዳሙ በቆዩባቸው ጊዜያት ያስተዋሉትን ሲገልጹም “የገዳማውያኑ ስሜት ልዩ ነው፡፡ የገዳማውያን አባቶችና እናቶች ደስታ ተመልክተናል፡፤ እንኳን እነሱ ለዘመናት የተቸገሩት ቀርቶ እኛም የተሰማን ስሜት መግለጽ ከምንችለው በላይ ነው፡፡ ደስታቸው አስደስቶናል፡፡ ሰዎች ለእግዚአብሔር በሰጡ ቁጥር የሚጎድልባቸው የሚመስላቸው አሉ፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር የተሻለ ነገር እንደሚሰጣቸው ማመን አለባቸው፡፡ ለእግዚአብሔር መስጠት አያጎድልም ይጨምራል እንጂ፡፡ የእኛን ደስታ ሌሎችም እንዲጋሩት እንፈልጋለን፡፡ ያደረግነው ነገር ትንሽ ቢሆንም ከእግዚአብሔር ጋር ከሆንክ ትረካለህ፡፡ ወደፊትም አቅማችን እያዳበርን ሌሎች ገዳማትን የመርዳት እቅድ አለን፡፡” በማለት ሁለቱ በጎ አድራጊ ወጣቶች ተናግረዋል፡፡

ማኅበረ መነኮሳቱ ስለተከናወነው የመንገድ ሥራ  ሲገልጹ “ብርሃን አየን፡፡ ለዘመናት የተቸገርንበትና ከአቅማችን በላይ የሆነውን ነገር እግዚአብሔር ደብቆ ያስቀመጣቸው ልጆቹን በመላክ አስወገደልን” ብለዋል፡፡

በተያያዘ ዜና ከአሰቦት ከተማ መገንጠያ እስከ ተራራው መውጫ ሥር ድረስ 12 ኪሎ ሜትር የሚፈጅ ሲሆን ገዳሙ ያለበትን የመንገድ ችግር ለመቅረፍ ከሚመለከተው ከክልሉ መንገዶች ባለስልጣን መሥሪያ ቤት ጋር  በመወያየት እንዲሁም አዲስ አበባ ከሚገኙ ምእመናን ጋር በመነጋገር  የመንገድ ሥራውን የሚቆጣጠርና የሚመራ አንድ ኮሚቴ አዋቅሮ በመንቀሳቀስ ላይ ይገኛል፡፡ በዚህም መሠረት በፌደራል መንገዶች ባለሥልጣን ሁሉን አቀፍ ተደራሽነት ያለው የገጠር መንገድ ፕሮግራም (Universal Rural Road Access Program) – URRAP መንገዱን ለመሥራት ባጠናው ጥናት መሠረት እሰከ 6 ሚሊዮን ብር እንደሚፈጅና 1 ሚሊዮን ብር ገዳሙ ከቻለ ቀሪውን ወጪ በመንግሥት እንደሚሸፈን በመግለጹ ስምምነት ላይ በመድረስ ሥራው ሊጀመር ችሏል፡፡

 

“ገዳሙም ባቋቋመው ኮሚቴ መሠረት ገንዘብ ከምእመናን በማሰባሰብ ላይ የሚገኝ ሲሆን የመንገዱ ሥራም የመጀመሪያውን ዙር በማጠናቀቅ ወደ ሁለተኛው ክፍል ተሸጋግሯል፡፡ ሥራውንም በቅርበት በመከታተል ላይ እንገኛለን፡፡ ገዳሙ ገንዘብ ለማሰባበሰብ ከፍተኛ ጥረት በማድረግ ላይ ሲሆን ከምእመናን  የታቀደውን ያህል ለማሰባበሰብ ባይቻልም በተገባው ቃል መሠረት የመጀመሪያ ዙር ክፍያ ተፈጽሟል፡፡ ቀጣዩንም ሥራ ለማከናወን የገንዘብ ማሰባሰቡ ይቀጥላል“ በማለት የኮሚቴው የቴክኒክ ክፍል ሓላፊ የሆኑት ኢንጂነር ዮሐንስ ዘውዴ  ገልጸዋል፡፡

 

በተጨማሪም ማኅበረ ቅዱሳን ገዳሙ ያለበትን የውኃ ችግር ለመቅረፍ በቅርቡ የባለሙያዎች ቡድን በመላክ አጥንቶ መመለሱን ከቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡

 

በ13ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የተገደመው የአሰቦት ደብረ ወገግ ቅድሥት ሥላሴና አቡነ ሳሙኤል ገዳም በተደጋጋሚ የእሳት ቃጠሎ ያጋጠመው ሲሆን እሳቱን ለመጥፋት በተደረገው ጥረት ውስጥ የተራራው አስቸጋሪነት ትልቁ ፈተና እንደነበር ይታወሳል፡፡

ledet04

የድንግሊቱም ስም ማርያም ነበር

ኅዳር 19 ቀን 2005 ዓ.ም.

በመ/ር ሰሎሞን መኩሪያ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ

ledet04በቤተ እስራኤል ስም ጠባይን፣ ግብርን፣ ሁኔታን እንደሚገልጥ ሁኖ ይሰየማል፡፡ ስለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም “ማርያም” የሚለውን ስያሜ ከማየታችን በፊት ስለ ድንግል ማርያም አባቶቻችን በነገረ ማርያም ያሉትን ጥቂት እንመለከታለን፡፡ “ነቢዩ ኢሳይያስ በትንቢቱ በም.1፥9 ላይ እንደተናገረ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር ዘርን ባያስቀርልን ኖሮ እንደ ሰዶም በሆንን ገሞራንም በመሰልን ነበር፡፡” እንዳለ በኦ.ዘፍ.ም.19፥1 ጀምሮ እንደተጻፈ የሰዶምና የገሞራ ሰዎች በበደላቸው ምክንያት እንደተደመሰሱ /እንደጠፉ/ እናነባለን፡፡ አዳምና ልጆቹ በሲዖል ባህር ሰጥመን እንዳንቀር እግዚአብሔር በቸርነቱ ንጽህት የሆነች ዘር መርገመ ሥጋ መርገመ ነፍስ የሌለባት በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስ እያማለደች የምታሰጥ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ባያስቀርልን ከእርሷም መርገመ ሥጋ መርገመ ነፍስን የሚያርቅ በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስ የሚያድል የባሕርይ አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ ተወልዶ በሞቱ ሞታችንን ባይደመስስ ወደ ሕይወት ባይመልሰን ኖሮ መኖሪያችን ሲዖል ነበር፡፡

 

ለፍጥረት ሁሉ መዳን ምክንያት ያደረጋት ንጽሕት ዘር እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ትውልዷ በአባቷ በኩል ከንጉሡ ከዳዊት ወገን ነው፡፡ በእናቷ በኩል ከሊቀ ካህናቱ ከአሮን ወገን ነው፡፡ የአባቷ ስም ቅዱስ ኢያቄም የእናቷ ስም ቅድስት ሐና  ይባላል፡፡ ሁለቱም በሕግ በሆነ ቅዱስ ጋብቻ ሲኖሩ ለብዙ ዘመን ልጅ አልነበራቸውም፡፡ ልጅ ይሰጠናል በማለት ተስፋ እግዚአብሔርን በጾም በጸሎት ደጅ እየጸኑ ኖሩ እንጂ፡፡ በዘመኑ ልጅ ያልወለደ ኀጢአተኛ፣ እግዚአብሔር የተጣላው ተደርጎ ይወሰድ ስለነበረ ወደ ቤተ እግዚአብሔር የሚያመጡትን መብዓ አይቀበሏቸውም፤ ይሰድቧቸው፣ ያሽሟጥጧቸውም ነበር፡፡ ይህንን ሁሉ ታግሰው ሲኖሩ እግዚአብሔር ትእግሥታቸውን ተመልክቶ የሚወልዷትን የድንግል ማርያምን ነገር በህልም ገለጸላቸው የእግዚአብሔርን ፈቃድ ሲጠብቁ እመቤታችን ነሐሴ 7 ቀን ተፀንሳለች፡፡ በተፀነሰች ጊዜ ብዙ ተአምራት ተደርጓል፡፡ የሃናን ማሕፀን እየዳሰሱ፡- ብዙ እውራን አይተዋል፣ ድውያን ተፈውሰዋል፣ ምውታን ተነሥተዋል፡፡ ይህንን የተመለከቱ አይሁድ ቅዱስ ኢያቄምን እና ቅድስት ሐናን በድንጋይ ወግረው በእሳት አቃጥለው ሊገድሏቸው በጠላትነት ሲነሡ የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ሊባኖስ ወደ ሚባል ተራራ ይዟቸው ወጣ፡፡ በዚያ ሳሉ በግንቦት 1 ቀን ከፀሐይ 7 እጅ የምታበራ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተወለደች፡፡ ጠቢቡ ሰሎሞን በመኀልይ በም.4፥8 ላይ እንደተናገረ “ሙሽራዬ ሆይ ከሊባኖስ ነይ…. ከአንበሶች ጉድጓድ ከነብሮችም ተራራ ተመልከች፡፡” እንዳለ ይህ ትንቢት ተፈጸመ በተወለደች በ8ኛው ቀን ስሟን “ማርያም” ብለው አወጡላት ለመሆኑ ማርያም ማለት ምን ማለት ነው?

 

ሀ. ማርያም ማለት ጸጋ ወሀብት ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ዳዊት በመዝ.126፥3 ላይ ልጆች የእግዚአብሔር ስጦታ ናቸው፡፡” ብሎ እንደተናገረ አባቷ ቅዱስ ኢያቄም እናቷ ቅድስት ሐና ከእግዚአብሔር የተሰጠችን ስጦታችን፣ ሀብታችን ናት ብለው “ማርያም” አሏት፡፡ ለጊዜው ለእናት እና ለአባቷ ስጦታ ሁና ትሰጥ እንጂ ለፍፃሜው ለፍጥረት ሁሉ እናት አማላጅ ሆና ከእግዚአብሔር የተሰጠች ናት በተለይ ለክርስቲያኖች በእምነት እናትነቷን እና አማላጅነቷን ለሚቀበሉ በዮሐንስ ወንጌላዊ አማካኝነት እናት ሁና የተሰጠች ልዩ ስጦታ ናት አምላካችን ክርስቶስ በቀራኒዮ አደባባይ በመስቀል ተሰቅሎ ቅዱስ ሥጋውን ቆርሶ ክቡር ደሙን አፍስሶ ለድኅነታችን እንደሰጠን ሁሉ እናቱንም እናት ትሁናችሁ ብሎ ሰጥቶናል፡፡” ዮሐንስ ወንጌላዊ ወደ ቤቱ እንደወሰዳት እኛም ወደ ቤተ ልቦናችን ልናስገባት ጣዕሟን በአንደበታችን ፍቅሯን በልቦናችን ልናሳድረው ያስፈልጋል፡፡ ዮሐ.19፥26 የድንግል ማርያም ጣዕሟ በአንደበታችን ፍቅሯ በልቦናችን ይደር፡፡ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤልም ከእግዚአብሔር ተልኮ ወደ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም መጥቶ እያመሰገናት እየተሳለማት የነገራት ነገር ቢኖር እርሷ “ምልዕተ ጸጋ ወክብር” እንደሆነች ነው፡፡ ሉቃ.1፥28 እንግዲህ መልአኩ ከእግዚአብሔር አግኝቶ የእመቤታችንን ነገር እንደነገረን የጐደለባት ጸጋ የሌለ እመቤት ናት እና እኛ ደግሞ ብዙ ነገር ጐድሎብናልና ከተትረፈረፈ ጸጋዋ እንድታድለን ምልዕተ ጸጋ ምልዕተ ውዳሴ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ልንማፀናት ይገባል፡፡ እመቤታችን ጸጋ በረከት ታድለን፡፡

 

ለ. ማርያም ማለት ፍፅምት ማለት ነው፡ “ፍፅምት” ማለት እንከንና ጉድለት የሌለባት ማለት ነው፡፡ እመቤታችን ለጊዜው መልክ ከደምግባት ጋር አስተባብራ በመገኘቷ ፍፅምት ተብላለች፡፡ እግዚአብሔር አምላክ በባሕርይው ቅዱስ ነው፡፡ ዘሌ.19፥2 ቅዱስ እና ንፁሐ ባሕርይ የሆነ እግዚአብሔር ዓለምን ለማዳን በወደደ ጊዜ አባ ሕርያቆስ በቅዳሴው እንደተናገረ “እግዚአብሔር በሰማይ ሁኖ ምሥራቁን እና ምዕራቡን ሰሜኑን እና ደቡቡን ዳርቻዎችን ሁሉ ተመለከተ እንዳንቺ ያለ አላገኝም የአንቺን መዓዛ ወደደ፤ ደምግባትሽን ወደደ፤ የሚወደውን ልጁን ወደ አንቺ ሰደደ” እንዲል፡፡ ንፁሐ ባሕርይ እግዚአብሔር ለማደሪያነት /ለተዋሕዶ/ እመቤታችንን መረጠ እርሷም ፍፅምት ናት የአዳም መርገም ያልወደቀባት /ጥንተ አብሶ/ የሌለባት ጠቢቡ ሰሎሞን በመኀል.4፥7 ላይ እንደተናገረ እንዲህ ብሎ “ወዳጄ ሆይ ሁለንተናሽ ውብ ነው ነውር የለብሽም፡፡” እንዲል እንኳን የአምላክ እናት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቀርቶ ወዳጆቹ ቅዱሳን እንኳን አካሄዳቸውን ከእግዚአብሔር ጋር ሲያደርጉ ከፍፁምነት ማዕረግ ይደርሳሉ ይህንንም ቅዱስ መጽሐፍ ይመሰክርላቸዋል፡፡ ለምሳሌ ኖኅ በትውልዱ ጻድቅ ፍፁምም ሰው ነበር  ዘፍ.6፥9፡፡ ኢዮብም ፍጹምና ቅን እግዚአበሔርንም የሚፈራ ከክፋትም የራቀ ነበር ኢዮብ 1፥1፡፡ ይላል፡፡ የኖኅን እና የኢዮብን አምላክ የወለደች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ፍፅምትነቷ አያጠራጥርም፡፡ የድንግል ማርያም ጸጋ በረክት ይደርብን፡፡

 

ሐ. ማርያም ማለት የሕያዋን እናት ማለት ነው፡፡ ዘፍ.3፥20 ላይ “አዳምም ለሚስቱ ሔዋን” ብሎ ስም አወጣ የሕያዋን ሁሉ እናት ናትና፡፡ ይላል በእርግጥ ሔዋን ለሕያዋን ሁሉ ማለትም ለፍጥረት ሁሉ እናት ናት ግን ፍጥረትን ሁሉ አስጐድታለች ማለትም አትብሉ ተብሎ ከእግዚአብሔር የታዘዘውን ዕፀ በለስን በልታ ለባሏ ለአዳም በማብላቷ በሰው ልጆች ላይ የሞት ሞት እንዲመጣ /እንዲፈርድባቸው/ ምክንያት ሁናለች ከእርሷ ምክንያተ ስህተትነት የተነሣ የገነት ደጃፎች ተዘጉ በምትገለባበጥ የኪሩብ ሰይፍ እንድትጠበቅ ሆነ፡፡ ዘፍ.3፥24 በዚህ የተነሣ በሰው ልጆች ላይ 5500 ዘመን ሞት ሰለጠነ፡፡ አዳም ግን “ሔዋንን” የሕያዎን ሁሉ እናት ብሎ በትንቢት የተናገረላት ሔዋንን ሳይሆን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ነው፡፡ ሊቁ ቅዱስ ኤፍሬም በውዳሴ ማርያም ዘሐሙስ “በእንተ ሔዋን ተዐፅወ ኆኅተ ገነት ወበእንተ ማርያም ድንግል ተርኀወ ለነ” ይላል ትርጉሙም “ስለ ሔዋን የገነት ደጅ ተዘጋ ዳግመኛ ስለ ድንግል ማርያም ተከፈተልን” ማለት ነው፡፡ ሔዋን ሕያዋንን ሁሉ አስጐዳች ዳግማዊት ሔዋን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ደግሞ ለሕያዋን ሁሉ እናት ሆና ፍጥረቱን ሁሉ ለማዳን ምክንያት ሆነች፡፡

 

ሕያዋን የሚባሉት ጥምቀተ ክርስትና ያላቸውን ወልድ ዋሕድ ብለው በልጇ በኢየሱስ ክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት የሚያምኑትን ክርስቲያኖችን ነው፡፡ እነዚህ ሕያዋን  ናቸው፡፡ ጌታ በቅዱስ ወንጌሉ “በወልድ ያመነ የዘለዓለም ሕይወት አለው ያላመነ ግን አሁን ተፈርዶበታል፡፡” እንዲል ዮሐ.3፥37 ደግሞም ሰው ሰው ተብሎ በሕይወት ለመኖር ከእናት ከአባቱ መወለድ ግድ እንዲሆንበት ክርስቲያንም ክርስቲያን ይባል ዘንድ ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ በጥምቀት መወለድ አለበት ዮሐ.3፥5፡፡ የእነዚህ እናታቸው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ናት፡፡ አንድም ሕያዋን የሚላቸው ለገነት ለመንግሥተ ሰማያት የሚያበቃቸውን የነፍስ ሥራ ሠርተው በጽድቅ የተሸለሙ ቅዱሳን ጻድቃን ሰማዕታት ናቸው የእነዚህ እናታቸው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ናትና ስማን “ማርያም” አሉት፡፡

 

መ. ማርያም ማለት ከፍጡራን ሁሉ በላይ ከፈጣሪ በታች የከበረች ደግ ፍጥረት ማለት ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላክ የሚታየውንና የማይታየውን ብዙ ፍጥረት ፈጥሯል ከእነዚህ ፍጥረታት መካከል ግን ሰው እና መላእክት ክብሩን እንዲወርሱ ስሙን እንዲቀድሱ ለይቶ ፈጥሮአቸዋል፡፡ ከሰው መላእክት በቅድስና ለእግዚአብሔር የቀረቡ ናቸው፡፡ ከእነዚህ መላእክት መካከል ስድስት ክንፍ ያላቸው ብዙ ዐይኖች ያሏቸው የእግዚአብሔርን ዙፋን የሚሸከሙ እግዚአብሔርም በዘፈቀደ ለወዳጆቹ ሲገለጽ የሚታይባቸው ክብር ያላቸው ናቸው፡፡ በፈጣሪያቸው ፊት ግን ሲታዩ ትእምርተ ፍርሐት አላቸው ከዙፋኑ የሚወጣው እሳት እንዳያቃጥላቸው በሁለት ክንፋቸው ፊታቸውን ይሸፍናሉ፤ ገጽህን ማየት አይቻለንም ሲሉ፤ በሁለት ክንፋቸው ከዳርቻ እስከ ዓለም ዳርቻ ይወጣሉ ይወርዳሉ ባህርይህን ተመራምሮ መድረስ አይቻልም ሲሉ፡፡ እንዲህ ባለ ፍርሐት ፈጣሪያቸውን “ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ እግዚአብሔር ጸባዖት ፍጹም ምሉዕ ሰማያተ ወምድረ ቅድሳተ ስብሐቲከ” እያሉ ያመሰግናሉ፡፡ ራዕ.4፣ ኢሳ.6 እነዚህ ከፍጡራን ሁሉ የከበሩ ለእግዚአብሔርም የቀረቡ ናቸው ከእነዚህ ግን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ትበልጣለች፡፡ ምክንያቱም እነርሱ እንዲህ ከሚንቀጠቀጡለት ከሦስቱ ቅዱስ አንዱን ቅዱስ ወልደ እግዚአብሔርን ዘጠኝ ወር ከ5 ቀን በማሕፀኗ የተሸከመች አዝላ የተሰደደች በማስተማር ዘመኑ ያልተለየች እስከ እግረ መስቀል ድረስ የነበረች የአምላክ እናት ናትና ስለዚህም ቅዱስ ኤፍሬም ሲናገር “ይእቲ ተዓቢ እም ኪሩቤል ወትፈደፍድ እም ሱራፌል እስመ ኮነት ታቦተ ለአሐዱ ዘእም ቅድስት ሥላሴ” ብሏል በእውነትም ከኪሩቤል እና ከሱራፌል ትበልጣለች ከቅድስት ሥላሴ አንዱን ወልደ እግዚአብሔርን በሕቱም ድንግልና ፀንሳ በሕቱም ድንግልና ወልዳዋለችና ይህ ጸጋ ለእመቤታችን እንጂ ከፍጡራን መካከል ለሌላ ለማንም አልተሰጠምና ከነገደ መላእክት ከደቂቀ አዳም በክብር የሚመስላት በጸጋ የሚተካከላት የለም፤ ከፍጡራን በላይ ያሰኛታል፡፡ “ከሴቶች ተለይተሽ የተባረክሽ ነሽ….. ካንቺ የሚወለደው ቅዱስ ነው፡፡ የልዑል እግዚአብሔርም ልጅ ይባላል፡፡” ሉቃ.1፥28፣ ሉቃ.1፥35 እንዲል፡፡

 

ሠ. ማርያም ማለት መርሕ ለመንግሥተ ሰማያት ማለት ነው /መንግሥተ ሰማያት መርታ የምታስገባ/ ማለት ነው፡፡ የቀደመው ፍጥረት የታደሰባት ወደ ቀደመ ርስቱ ወደ መንግሥተ ሰማያት ለመግባት ምክንያተ ድሂን የሆነችው እመቤታችን ድንግል ማርያም ናት ዛሬም ያለው ፍጥረት ወደ መንግሥተ ሰማያት ለመግባት የድንግል ማርያም ምልጃ ያስፈልገዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያን የእመቤታችንን መርቶ መንግሥተ ሰማያት የምታስገባ የመሆኗን ነገር በምሳሌ እንዲህ ስትል ታስተምራለች፡፡ በዘፀ.ም.32 እና 34 ላይ ተጽፎ እንደምናገኘው ሙሴ በደብረ ሲና 40 መዓልት 40 ሌሊት ከጾመ ከጸለየ በኋላ እግዚአብሔር ተቀብሎ ከተራራው ሲወርድ እስራኤል ጣዖት አቁመው ሲሰግዱ ተመለከተ በዚህ ጊዜ ፍቅረ እግዚአብሔር ቢያቃጥለው በፅላቱ ጣዖቱን መታው ፅላቱ ተሰበረ ጣዖቱ ደቀቀ፡፡ ወደ እግዚአብሔር ሲያመለክት ከማይነቅዝ እንጨት ሠርቶ ወደ ተራራው እንዲወጣ በዚያም እንደ ቀድሞው እንዲጾም እንዲጸልይ እግዚአብሔር አዘዘው እርሱም እንደታዘዘው አደረገ እግዚአብሔርም በተሰወረች ጣት ትዕዛዛቱን ጻፈበት ለሙሴም ሰጠው ሙሴም ይህንን ይዞ ከተራራው ሲወርድ ብርሃን ተሳለበት እስራኤል በዚች ፅላት እየተመሩ የዮርዳኖስን ባህር ከፈሉ ኢያሱ.3፥14-17 የኢያሪኮን ቅፅር ናዱ /አፈረሱ/ ኢያ.6፥8 ምድረ ርስት ከነዓን ገብተው ርስት ተካፈሉ፡፡ በዚህ ምሳሌ የቀደመው ከእግዚአብሔር ዘንድ ለሙሴ የተሰጠው የእንቁ ፅላት የአዳም የፅላቱ መገኛ ከእግዚአብሔር እንደሆነ ሁሉ ለአዳምም እናትና አባት መገኛ የሚሆን የለውም ወድቆ መሰበሩ ሕግ ትዕዛዝ በመተላለፉ ከፈጣሪው መለየቱን ያመለክታል፡፡ ፅላቱ እንደተሰበረ ይቅር እንዳላለ አዳምም እንደወጣ ይቅር አላለም በንስሓው ተቀብሎታልና፡፡ ሁለተኛይቱ ፅላት እመቤታችን ሙሴ ሠርቶ መውሰዱ እመቤታችን በዘር መገኘቷን ከቅድስት ሐና ከቅዱስ ኢያቄም መወለዷን ያመለክታል፡፡ ከማይነቅዝ እንጨት መሥራቱ እመቤታችን በሐልዮ /በማሰብ/ በነቢብ /በመናገር/ በገቢር /መሥራት/ ኀጢአት እንዳልፈጸመች ንፅናናዋን ቅድስናዋን ያመለክታል፡፡ በፅላቱ ላይ በእግዚአብሔር ጣት የተጻፈ የእግዚአብሔር ቃል ነው፡፡ በማሕፀነ ድንግል የተቀረጸው የአብ አካላዊ ቃል ኢየሱስ ክርስቶስ እንደሆነ ያመለክታል፡፡ ዮሐ.1፥1 “በመጀመሪያ ቃል ነበረ ቃልም እግዚአብሔር ነው” ዮሐ.1፥14 የቃል ሥጋ ሆነ በእኛም አደረ” እንዳለ፡፡ በዚያች ፅላት እስራኤል ባህር እንደተከፈለላቸው፣ ቅፅር እንደተናደላቸው ተመርተው ርስት እንዲወርሱ ጥንተ ጠላታትን ዲያብሎስ ተሸንፎ በእመቤታችን በተሰጣት ቃል ኪዳን አማላጅነት ከገቡ መውጣት ካገኙ ማጣት የሌለባት መንግሥተ ሰማያትን ለመውረስ እድል አገኘን፡፡ ከብዙ በጥቂቱ ከላይ የተጠቀሰውን አልን እንጂ ስለ እመቤታችንስ የተነገረው ብዙ ነው፡፡ የድንግል ማርያም ጣዕሟ በአንደበታችን ፍቅሯ በልቡናችን ይደርብን በአማላጅነቷ ለርሥተ መንግሥተ ሰማያት ታብቃን አሜን፡፡

dn. reda wube

ዲያቆን ረዳ ውቤ አረፉ

ኅዳር 17 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ


dn. reda wubeበሲዳሞ  ክፍለ ሀገር፣ ቡሌ ወረዳ በሚገኘው ጎንፈራ ቀበሌ፥ ከወላጅ አባታቸው አቶ ውቤ አብዲና ከእናታቸው ከወ/ሮ መሰለች ተመስገን፥ መጋቢት 5 ቀን 1955 ዓ.ም የተወለዱት ዲ/ን ረዳ ውቤ፤ ባደረባቸው ሕመም ምክንያት በልዩ ልዩ የሕክምና መስጫ ተቋማት ሲረዱ ቆይተው  በ50 ዓመታቸው ኅዳር 10 ቀን 2005 ዓ.ም ከዚህ ዓለም በሞተ ሥጋ ተለይተው፥ ኅዳር 11 ቀን 2005 ዓ.ም በቡራዩ ፄዴንያ ስመኝ ማርያም ገዳም ሥርዓተ ቀብራቸው ተፈጽሟል፡፡

 

ዲያቆን ረዳ ውቤ ከልጅነት ዕድሜያቸው አንሥቶ ለቤተ ክርስቲያን  ትምህርትና አገልግሎት ከነበራቸው ጽኑ ፍቅር የተነሣ፥ ከመምህራቸው አባ ኀይለ ማርያም ግብረ ዲቁናን ተምረው በ1969 ዓ.ም በወቅቱ የሲዳሞ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ከነበሩት ብፁዕ አቡነ በርቶሎሚዎስ መዓረገ ዲቁናን ተቀብለዋል፡፡ከዚህ በኋላ ከ1969 እስከ 1977 ዓ.ም የይርጋለም ደብረ መዊዕ ቅዱስ ሚካኤል ሰንበት ትምህርት ቤትን በመመሥረትና ለአምስት ዓመታት በሰብሳቢነት፣ እንዲሁም ሰንበት ትምህርት ቤቱን በመወከል በደብሩ የሰበካ ጉባኤ በጸሓፊነት አገልግለዋል፡፡ ዲያቆን ረዳ ከ1978 እስከ 1980 ዓ.ም በባሕር ዳር ፖሊ ቴክኒክ ኢንስቲቲዩት በነበራቸው የትምህርት ቆይታ፥ በባሕር ዳር ፈለገ ገነት ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ትምህርት ቤት በአባልነት ተመዝግበው የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች  ወደ ቤተ ክርስቲያን እንዲሄዱና በሰንበት ትምህርት ቤት እንዲሳተፉ፡ አልፎም ዛሬ በመላ ሀገሪቱ እየተካሄደ ላለው የግቢ ጉባኤ መጀመር ምክንያት ለመሆን የበቁ ሰው ናቸው፡፡

 

በዲ/ን ረዳ ውቤ ሕይወትና በአገልግሎታቸው ዙሪያ ከተዘጋጀው የግለ ሕይወት ታሪካቸው ለመረዳት እንደተቻለው፡- የመጀመሪያዎቹን ክርስቲያኖች የአንድነት ኑሮን መሠረት በማድረግ በተቋቋመው የጽርሐ ጽዮን ዘተዋሕዶ አንድነት ኑሮ ማኅበርን ከጥቅምት 2 ቀን 1990 ዓ.ም ጀምሮ በመቀላቀል ነፍሳቸው ከሥጋቸው እስክትለይ በዚያው ቦታ ቆይተዋል፡፡ በዚሁ ቆይታቸውም ማኅበሩን በልዩ ልዩ ሓላፊነቶች ያገለገሉ ሲሆን ማኅበሩ ባካሄዳቸው 15 ዙር የሰባክያነ ወንጌል ሥልጠናዎች ላይ በመምህርነት ተሳታፊ ሆነዋል፡፡ በተጨማሪም ከ1990 ዓ.ም. ጀምሮ እስከ ዕለተ ረፍታቸው የማኅበሩ የሰባክያነ ወንጌል ማሠልጠኛ ትምህርት ክፍል ሓላፊ በመሆን አገልግለዋል፡፡

 

መላ ዘመናቸውን ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የሰጡት ዲያቆን ረዳ ውቤ  የሳንባ፣ የልብና የጨጓራ ሕመማቸውን ታግሰው ቤተሰባቸውና ማኅበሩ እንዳይጨነቅ ሕመምተኛ ሳይመስሉ የተጣለባቸውን ሓላፊነት በትጋት ተወጥተዋል፡፡ዲያቆን ረዳ ባለትዳርና የአራት ልጆች አባት ነበሩ፡፡

በእኛ ዘመን ምንጮቻችን እንዳይነጥፉ

ኅዳር  17 ቀን 2005 ዓ.ም.


የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ዘርፈ ብዙ መንፈሳዊ አገልግሎት መሠረት የሆኑት፤ የአባቶች ካህናት፣ ሊቃውንት መምህራን፣ ጳጳሳት የአገልጋዮቿ መፍለቂያ፤ ለዘመናት የማይነጥፉ ምንጮች ሆነው የኖሩት አብነት ትምህርት ቤቶቻችን፤ በዚህ ዘመንና ትውልድ ህልውናቸውን ጥያቄ ውስጥ ያስገባ ፈተና እንደተጋረጠባቸው የዐደባባይ ምስጢር ከሆነ ቆይቷል፡፡

 

ከቅዱስ ሲኖዶስ ጀምሮ የሚመለከታቸው የቤተ ክርስቲያን አካላት እንዲሁም ቅን አሳቢ እውነተኛ ልጆቿ ሁሉ ለጉዳዩ ትኩረት ሰጥተው የተግባራዊ መፍትሔው አካል በመሆን ሲንቀሳቀሱም ይታያል፡፡

 

እንዲህም ሆኖ ግን ከጊዜ ወደ ጊዜ ችግሩ እየተደራረበ መጥቶ በወቅቱ መሠረታዊ ለውጥና የተሻለ እድገት የሚያስገኝ መፍትሔ ባለመሰጠቱ የአብነት ትምህርት ቤቶቻችን ፈተና ከፍቷል /ተባብሷል/፡፡

 

የትምህርት አሰጣጥ ሥርዓቱ ጊዜና አካባቢያዊ ሁኔታዎችን ከመንፈሳዊና ቁሳዊ ሀብቶች ጋር በማገናዘብ ዘመኑን የዋጀ እንዲሆን አለመደረጉ፤ በተቀላጠፈና ወጥ በሆነ መንገድ ተደራጅቶ አለመሰጠቱ፤ የአብነት ትምህርት ቤቶች አደረጃጀት የመማሪያ ክፍሎች፣ የትምህርቱ መርጃ መሣሪያዎች፣ መጻሕፍት ወዘተ በፍጹም አለመሟላታቸው፤ የሊቃውንት መምህራኑ የኑሮ ችግርና በቂ መተዳደሪያ ድጋፍ አለማግኘት፤ የደቀ መዛሙርቱ ለረኃብና ለዕርዛት መዳረግ፤ መጠለያ ማጣት፤ የጤና ክብካቤና ትምህርት የሚያገኙበትና በዝቅተኛ ደረጃም ቢሆን የሕክምና አገልግሎት አለመኖር፤ በአንጻሩ ደግሞ ይህንን ሁሉ ችግርና መከራ ተቋቁመው ለዓመታት ደክመው ከሊቃውንት መምህራን አባቶቻቸው የዕውቀት ማዕድ የቀሰሙትን ዕውቀትና ሙያ ለቤተ ክርስቱያኒቱ አገልግሎት የሚያውሉበት የሥራ ዋስትና ማጣታቸው ከሌሎችም ውጫዊ ተግዳሮቶች ጋር ሲደመር ለመማር ማስተማሩ ትልቅ ፈተና ስለሆነ ወዘተ…. አፋጣኝ ተግባራዊ መፍትሔ የሚፈልግ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን የአብነት ትምህርት ሕልውናና ቀጣይነት ላይ የተደቀነ ገሐድ አደጋም ስጋትም ነው፡፡

 

ሁለንተናዊ ፈተናዎቹን በሚፈታ መልኩ መሠረታዊ መፍትሔ በአፋጣኝ ባይታይም፤ ይህንን ችግር በመቅረፍ የአብነት ትምህርት ቤቶቻችንን ከተደቀነባቸው አደጋ ለመታደግ ተስፋ ሰጪ ጥረቶች እየተደረጉ እንደሆነ ይታወቃል፡፡

 

ባለፈው የጥቅምት ወር 2005 ዓ.ም በተካሄደው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ፤ የአብነት ትምህርት ቤቶችን ለማጠናከር የተወሰነው የዐሥር ሚሊዮን ብር በጀት ለችግሩ የተሰጠውን ትኩረት የሚያመለክት፤ ለአስተማማኝ ቀጣይነቱም የተስፋ ብርሃን የሚፈነጥቅ ነው፡፡

 

ይህንን በድርሻው ለማጠናከር በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል አማካኝነት፤ “የጥንቱ ከሐዲሱ ጋር በደጃችሁ አለ” በሚል መሪ ቃል ኅዳር 2 ቀን 2005 ዓ.ም በጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ ይፋ የሆነው፤ “አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ የነጻ ትምህርትና ሥልጠና ዕድል” የአብነት ትምህርቱን ዘመኑን በዋጀ መልኩ በትውልዱ ቀጣይነት እንዲኖረው የሚያስችል መርሐ ግብር ነው፡፡

 

እንዲህ ዓይነቶቹ ተጠቃሽ የመፍትሔ እርምጃዎች ለቤተ ክርስቲያን የአብነት ትምህርት ቀጣይነት ዋስትና ሰጪ ጥረቶች ናቸው፡፡ አፈጻጸማቸውን በተመለከተም የተቀናጀ አሠራር፤ የቅርብ ክትትልና ቁርጠኛ አገልግሎት ይፈልጋሉ፡፡ ችግሩ እየከፋ ከመምጣቱ አኳያም ቀዳሚ ትኩረትና አፋጣኝ የተግባር ክንውን እንደሚያስፈልግ የታወቀ ነው፡፡

 

አብነት ትምህርት ቤቶች ወቅቱና ትውልዱን እንዲሁም አካባቢያዊ ሁኔታዎችን በማገናዘብ ከዘመናዊው ትምህርት ጋር ተቀናጅተው የሚያድጉበትና የሚቀጥሉበትን መፍትሔ መፈለግና በተግባር ማረጋገጥ ለነገ የሚባል ጉዳይ አይደለም፡፡

 

በተለይም በገጠሩ አካባቢ የሕዝቡ የኑሮ ሁኔታና ለአብነት ትምህርቱ ያለው አመለከካከት እየተለወጠ መምጣቱን ተከትሎ ለመምህራኑና ለተማሪዎቹ የሚያደርገው ድጋፍ መቅረት ዐቢይ ችግር ነው፡፡ ይህንን ችግር ተረድቶ መፍትሔ የሚሆኑ ተተኪ አሠራሮችን መቀየስና በአፋጣኝ ተግባራዊ ማድረግ የግድ ይላል፡፡ ደቀመዛሙርቱ የነገይቷን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት መስፋፋት ተስፋ አድርገው፤ ለዓመታት በችግርና መከራ ውስጥ እያለፉ በአብነት ትምህርቱ የቀሰሙትን ዕውቀትና ሙያ ይዘው ከተመረቁ በኋላ፤ በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ተመድበው መተዳደሪያ አግኝተው ቤተ ክርስቲያንንም የሚያገለግሉበት አስተማማኝ የሥራ ዋስትና ሊሰጣቸው ይገባል፡፡ ዓለም አቀፋዊውንና አካባቢያዊ ሁኔታዎችን የሚገነዘቡበት፣ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ አጠቃላይ ለውጦችን በማስተዋል በቀላሉ ተረድተው የሚያዘጋጁበትና በነገ አገልግሎታቸው የትውልድ መሪ የምእመናን አለኝታ ሆነው እንዲቀጥሉ የሚያስችሏቸውን ተጨማሪ ትምህርቶች የሚያገኙበትን መንገድ ማመቻቸትና ተግባራዊ ማድረግ አስፈላጊ ነው፡፡

 

የአብነት ት/ቤቶች ባልተስፋፉባቸው አህጉረ ስብከት የገጠርና ጠረፋማ አካባቢዎችም፤ የወቅቱን ተጨባጭ ሁኔታ ያገናዘቡና በሚገባ የተደራጁ የአብነት ትምህርት ቤቶችን ማቋቋም ያስፈልጋል፡፡ በየአካባቢው ቋንቋ ሊያስተምሩና ሊያገለግሉ የሚችሉ መምህራነ ወንጌልና አገልጋይ ካህናትን ማውጣት (ማፍራት) ቅድሚያ ከሚሰጣቸው ተግባራት አንዱ ነው፡፡

 

አለበለዚያ አገልጋይ ካህናትና መምህራነ ወንጌል በማጣት ከዕለት ወደ ዕለት የሚዘጉት በየገጠሩና በየበረሐው እንዲሁም በየጠረፉ የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት ቁጥር በከፍተኛ ፍጥነት እየጨመረ መምጣቱ አይቀርም፡፡ ከቤተ ክርስቲያን እቅፍ እየወጡ በሌሎች የሚነጠቁት ምእመናንም ቁጥር የዚያኑ ያህል እየጨመረ እነሱን ለመታደግ አስቸጋሪ ይሆናል፡፡

 

ተተኪ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እያነሱ፣ በየገዳማቱ የሚያገለግሉ እውነተኛ መነኰሳት እየቀነሱ፤ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም በሁለንተናዊ መንፈሳዊ አገልግሎቷ እየተዳከመች፤ በማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዘርፍ የሚኖራት ተሳትፎ እየጠበበ፤ እስተዳደራዊ መዋቅሯና አሠራሯ ብቃት እያነሰው፤ ምእመናኗም በመንፈሳዊ ሕይወታቸው፣ በዕለት ተዕለት ኑሮአቸውና ማኅበራዊ ግንኙነታቸው የሚያበረታቸው፣ የሚመክራቸው፣ የሚከታተላቸው፣ የሚያጸናቸውና የሚያመላክታቸው እያጡ በዘመኑ ሥልጣኔ የባሕል ወረርሽኝ እየተዋጡ፣ ለማንነት ጥያቄያቸው ምላሽ እያጡ፣ ለሃይማኖታዊና ማኅበራዊ ቀውስ እየተዳረጉ ይመጣሉ፡፡ የዚህ ሁሉ ድምር ውጤት የሚያስከትለውን የከፋ ችግር ከወዲሁ ለመገንዘብ ከሁላችንም የሚሰወር እንዳል ሆነ ይታወቃል፡፡

 

ስለዚህ ዘርፈ ብዙ ለሆነው የቅድስት ቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊ አገልግሎት መሠረት የሆኑት፤ የሊቃውንቱ፣ የጳጳሳቱ፣ የአገልጋይ ካህናቱ፣ የመምህ ራነ ወንጌሉ ሁሉ መፍለቂያ ምንጮች አብነት ትምህርት ቤቶቻችን በእኛ ዘመንና ትውልድ ሳይነጥፉ እንዲቀጥሉ በተጠናና ችግር ፈቺ በሆነ መንገድ ጥረት የሚያደርጉትን አካላት በሚቻለን ሁሉ በማገዝ ከሁላችንም ተጨባጭነት ያለው ተሳትፎ ይጠበቅብናል፡፡

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

abune petros statute

የብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ሐውልት ለጊዜው ከቦታው ይነሣል

ኅዳር 15 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

የአዲስ አበባ ከተማ ትራንስፖርት ችግርን ለመቅረፍ እንዲያስችል በሚዘረጋው የቀላል ባቡር መሥመር ዝርጋታ ምክንያት የብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ሐውልት እንደሚነሣ የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን አስታወቀ፡፡

abune petros statute

አቶ አበበ ምሕረቱ የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን የኮምኒኬሽን አገልግሎት ክፍል ሓላፊ የሐውልቱ መነሣት ያስፈለገበት ዋነኛ ምክንያት ምን እንደሆነ ሲገልጹ “በቀላል ባቡር መስመር ዝርጋታ ምክንያት መንገዱ ከዳግማዊ አፄ ምኒልክ አደባባይ ጀምሮ ወደ አውቶቡስ ተራ የሚወስደው መንገድ አትክልት ተራ ድረስ ባቡሩ በዋሻ ውስጥ ነው የሚያልፈው፡፡ በተጨማሪም የባቡሩ መስመር  ከምኒልክ አደባባይ ወደ ሽሮ ሜዳ ይዘረጋል፡፡ እንደሁም ከአውቶቡስ ተራ ወደ ቅድስት ልደታ ለማርያም የሚታጠፈው መስመር መነሻም ነው፡፡ ስለዚህ በአሁኑ ወቅት ከማዘጋጃ ቤት አጥር ጀምሮ ወደ ትግበራ የተገባበት ሁኔታ ላይ እንገኛለን፡፡ ሥራው ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ሀውልት ሲደርስ ስዊድን አገር የሚገኘውና ከፍተኛ ልምድ ያለው ዓለም አቀፍ አማካሪ ድርጅት ሥራውን በበላይነት የሚቆጣጠረው ሲሆን በሚያስመጣቸው ባለሙያዎች አማካይነት በክብርና በጥንቃቄ ሐውልቱን አንሥቶ የዋሻው ግንባታ እንደተጠናቀቀ አንዲትም ሣ/ሜትር ሳይዛነፍ እንደነበረ በቦታው ላይ በክብር እንዲያስቀምጥ ይደረጋል፡፡ ሐውልቱ የሀገር ቅርስና ሀብት ነው፤ ለዚህም ከፍተኛ ጥንቃቄ የተሞላበት ሥራ ይሠራል፡፡” ብለዋል፡፡

 

ፕሮጀክቱ የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን ብቻውን የሚያከናውነው ሳይሆን የአዲስ አበባ የጽዳትና ውበት ኤጀንሲ፤ የአዲስ አበባ ቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለስልጣን፤ ባሕልና ቱሪዝም ቢሮዎች፤ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር እንዲሁም የሃይማኖት አባቶች ጋር በመሆን እንደሚከናወን የገለጹት የኮርፖሬሽኑ የኮምኒኬሽን አገልግሎት ክፍል ሓላፊው  በጉዳዩ ላይ ሰፊ ውይይት በማድረግ ወደ ትግበራ እንደተገባ አጽንኦት ሰጥተው ተናግረዋል፡፡

 

“ሐውልቱ ተነሥቶ የት ነው የሚቆየው?” በማለት ላቀረብንላቸው ጥያቄ ምላሽ ሲሰጡም “ሐውልቱ በክብር ከተነሣ በኋላ ባለሙያዎቹ በሚያቀርቡት ጥናት መሠረት ባለ ድርሻ አካላት ተወያይተው በሚዘጋጀው አስተማማኝና ምቹ ሥፍራ ላይ እንዲቀመጥ ይደረጋል፡፡ በመጨረሻም በክብር ወደ ቦታው ይመለሳል” ብለዋል ፡፡

 

የዳግማዊ አፄ ምኒልክ ሐውልት በተመለከተም ”አሁን ባለው ዲዛይን መሠረት ሐውልቱን ስለማይነካው አይነሣም” በማለት ምላሻቸውን ሰጥተዋል፡፡

 

“ይህንን ጉዳይ ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አሳውቃችኋል?” ብለናቸውም “ፕሮጀክቱ የሁላችንም ነው፡፡ የሀገር ነው፡፡ ጉዳዩ ይመለከታቸዋል ለተባሉት አካላት ሁሉ አሳውቀናል፡፡” በማለት የመለሱ ሲሆን ወደፊትም ተቀራርበው እንደሚሠሩ ገልጸዋል፡፡

 

“ሌላ ዲዛይን ለመሥራት ለምን አልተሞከረም?” ላልናቸው ሲመልሱም “ዲዛይኑ ማእከላዊውን መንገድ ይዞ ነው የተሠራው፡፡ ይህንኑ ተከትሎ ይከናወናል፡፡”በማለት መልሰዋል፡፡

 

በመጨረሻም “ሐውልቱ ከተነሣ በኋላ ወደ ቦታው ለመመለሱ ሓላፊነቱን ማነው የሚወስደው?” ብለን ለጠየቅናቸው  “መንግሥት የህዝብን ችግር ለመፍታት በሚያደርገው ጥረት ውስጥ ሁሉም ሀላፊነቱን ወስዶ የሚሰራ ይሆናል፡፡ ባለ ድርሻ አካላቱም የመንግሥትን ሥራ የሚያስፈጽሙ በመሆናቸው ሓላፊነት አለባቸው፡፡ ስለዚህ ሁሉም ሓላፊነት አለበት” ብለዋል፡፡

የማኅበሩ የቴሌቪዥን ፕሮግራም ተራዘመ

ኅዳር 11 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

የማኅበረ ቅዱሳን የኅትመትና ኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ዋና ክፍል በኢቢኤስ የቴሌቪዥን መርሐ ግብር ለመጀመር ከፍተኛ ጥረት እያደረገ እንደሚገኝ ይታወቃል፡፡ ነገር ግን በእኛ በኩል ዝግጅታችንን ለመጀመር ዝግጁ ሆነን እየተጠባበቅን የምንገኝ ሲሆን ከኢቢ ኤስ ቴሌቪዥን  በኢትዮጵያና በመካከለኛው ምሥራቅ አገራት የጀመረው ስርጭት ከኅዳር 5 ቀን 2005 ዓ.ም. ጀምሮ ካልታወቀ አቅጣጫ በተደረገ ከፍተኛ የሳተላይት ሲግናል ማዛባትና እቀባ ወይም “ጃሚንግ” እክል እንደደረሰበት አስታውቋል፡፡ በመሆኑም ስርጭቱ እንደተስተካከለ የማኅበረ ቅዱሳን ቴሌቪዥን መርሐ ግብር የሚቀጥል ሲሆን በትእግሥት እንድትጠባበቁን በአክብሮት እንጠይቃለን፡፡