2 (2)

የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ የድኅረ ምረቃ መርሐ ግብር ጀመረ

ጥቅምት 29 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ


2 (2)ቅዳሜ ጥቅምት 24 ቀን 2005 ዓ.ም በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ የመሰብሰቢያ አዳራሽ፤ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የኮሌጁ የቦርድ አባላት፣ የአስተዳደር ሠራተኞች፣ መምህራንና ተማሪዎች እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት በጸሎት በተከፈተው ጉባኤ፥ ኮሌጁ የሁለተኛ ዲግሪ መርሐ ግብር መጀመሩ በይፋ ተበስሯል፡፡

 

የእንኳን ደህና መጣችሁና የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ የቅድሰት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ሓላፊና፥ የቅዱስ5 ሲኖዶስ አባል፤ ኮሌጁ፥ ከጊዜ ወደ ጊዜ በእግዚአብሔር ፈቃድ እያደገ ከፍተኛ የነገረ መለኮት ኮሌጅ ለመሆን መብቃቱን አውስተው፥በተለይ አፄ ኀ/ሥላሴ ለኮሌጁ ያበረከቱትን አስተዋጽኦ ሲናገሩ፡- “አሁን ኮሌጁ የሚገኙበትን ቦታ፥ የቤተ ክርስቲያንና የሀገሪቱ አባት የነበሩት ግርማዊ ቀዳማዊ አፄ ኀይለ ሥላሴ ለመንፈሳዊ ትምህርት ከነበራቸው ቅን አስተሳሰብ በመነጨ ቦታውን ‘የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ትምህርት ቤት’ ተብሎ እንዲሰየምና አገልግሎት እንዲሰጥ አበርክተዋል፡፡ ግርማዊነታቸው ለቤተ ክርስቲያኒቱ በሠሯቸው በጎ ሥራቸው ሲታሰቡ ይኖራሉ፡፡ ”በማለት ገልጸው፥ኮሌጁ የመክፈቻ ንግግራቸውን ያደረጉት ከጥቅምት 24 ቀን 2005 ዓ.ም. ጀምሮ በሲስተማቲክ ቲዎሎጂ የሁለተኛ ዲግሪ መርሐ ግብር ለመጀመር እንደተቻለ አስታውቀዋል፡፡

 

ከብፁዕነታቸው የመክፈቻ ንግግር ተከትሎ ስለኮሌጁ ታሪካዊ ዳሰሳ ያቀረቡት ዶ/ር አባ ኀይለ ማርያም መለሰ የኮሌጁ 4 (2)ምክትል ዋና ዲ/ን፡- “የትምህርት መድረክ የጥበብ መደብር ነው፡፡ ለአያሌ ዘመናት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ብቸኛዋ የእውቀት ቀንዲል አብሪ ሆና ቆይታለች፡፡ ይህ የተቀደሰ ተልዕኮዋም እየሰፋና እያዳበረ ሄዶ ለዛሬ በቅተናል፡፡ ለዚህም አንዱ ዓይነተኛ መሣሪያ ይህ ከፍተኛ የትምህርት ማእከል ነው፡፡ በእግዚአብሔር ስም የተመሠረተ እውቀት መንፈሳዊ እየተስፋፋ በሄደ ቁጥር፥ የቤተ ክርስቲያናችን ክብር፣ የሃይማኖታችን ጽናት፣ የሀገራችን ፍቅር፣ ሰላምና አንድነት ይጠበቃል ይጠነክራል ይልቁንም ትውልዱ እግዚአብሔርን የሚፈራ ግብረ ገብነት ያለው ይሆናል፡፡

 

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከአንድ ሺህ አምስት መቶ ዘመን በላይ በሀገራችን በኢትዮጵያ የትምህርት ማዕከል ሆኖ ቆይታለች ይኸንኑ ለረጅም ዘመን በበላይነትና በብቸኝነት የቆየ መንፈሳዊ ትምህርት በዘመናዊው የማስተማር ስልት (ዘይቤ)  ማከናወን ይቻል ዘንድ በ1934 ዓ.ም. የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት ግርማዊ ቀዳማዊ ዓፄ ኃይለ ሥላሴ፥ የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅን ‘የካህናት ፎረም’ በሚል ስያሜ በቤተ መንግሥታቸው መሠረቱት፣” በማለት ስለ ታሪካዊ አመሠራረቱ ካወሱ በኋላ በ1935 ዓ.ም. የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ የተመሠረተበት የገነት ልዑል ቤተ መንግሥት አሁን ወዳለበት ቦታ ተዛወሮ በዚሁ ዘመን ግርማዊነታቸው የቅድስት ሥላሴን መንፈሳዊ ትምህርት ቤት ሕንፃ የመሠረት ድንጊያ እንዳስቀመጡ ገልጸዋል፡፡

 

በስተመጨረሻም በዛሬው እለት ለተሰባሰብንበት የድኅረ ምረቃ መርሐ ግብር ኮሌጁ ለዚህ መብቃቱ ለመላው የቤተ ክርስቲያን አማኞችና2 (1) ወዳጆቿ ታላቅ የምሥራችና ደስታ ነው፡፡ ይህን መርሐ ግብር ለመጀመር ከፍተኛ አባታዊ አመራር የሰጡንን የኮሌጃችንን ኃላፊ ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስን፣ እንዲሁም የአመራር ቦርዱን፣ መምህራንና የቢሮ ሠራተኞችን ለዚህ ስኬት በመሥራታቸው ልባዊ ምስጋናዬን አቀርባለሁ” በማለት ንግግራቸውን አጠናቀዋል፡፡

 

ከዶክተር አባ ኀይለማርያም ንግግር ቀጥሎ በመምህር ፍስሐጽዮን ደሞዝ የኮሌጁ ምክትል አካዳሚክ ዲን ስለኮሌጁ አካዳሚክ እድገትና ስለድህረ ምረቃ መርሐ ግብር አጀማማር ሪፖርት ቀርቧል፡፡

 

6‘‘ኮሌጁ ከተከፈተ ጊዜ ጀምሮ ለረጅም ዓመታት ደቀመዛሙርትን ያሰለጥን የነበረው በዲፕሎማ እና በዲግሪ መርሐ ግብሮች ሲሆን ከ2002 ዓ.ም ጀምሮ ግን በልሳነ ግእዝ ዲፕሎማ፣ በርቀት ሰርተፍኬት፣ በድህረ ምረቃ ዲፕሎማ(PGD) እና በዘንድሮው የትምህርት ዘመን ደግሞ ለመጀመሪያ ጊዜ የድህረ ምረቃ የሁለተኛ ዲግሪ መርሐ ግብሮችን ሊጀምር ችሏል፡፡ ከነዚህ ፕግራሞች በተጨማሪ በቀጣይ በርቀት ትምህርት ዲፕሎማ መርሐ ግብርን ለማስጀመር አስፈላጊውን ቅድመ ዝግጅት አጠናቅቋል፡፡’’በማለት የተናገሩት  ምክትል አካዳሚክ ዲኑ የሁለተኛ ዲግሪ መርሐ ግብር ለመጀመር ያስፈለገበትን ምክንያት ሲያብራሩ አራት ነጥቦችን ጠቅሰዋል፡፡ እነርሱም

 

1ኛ. የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በ21ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ዶግማዋን፣ ቀኖናዋን፣ ሥርአቷን፣ ትውፊቷን እና ባሕሏን እንዲሁም አንድነቷን ጠብቃ ወደፊት እንድትራመድ የሚያስችላት ትውልድ ተሻጋሪ የሆነ ከፍተኛ የጥናትና ምርምር ተቋም እንዲኖራት ለማስቻል፣

 

2ኛ ቤተ ክርስቲያናችን ከፊቷ ከተጋረጡባት ተግዳሮቶች ማለትም ከዘመናዊነትና ከሉላዊነት (globalization) ራሷን የምትከላከልበት በነገረ መለኮት ትምህርት የበሰሉ መምህራንና ደቀ መዛሙርትን ለማፍራት፡

 

3ኛ. ቤተ ክርስቲያናችን በሀገር ውስጥ እና ከሀገር ውጪ ካሉዋት ተከታዮች አንፃር ሲታይ ያልዋት ከፍተኛ የነገረ መለኮት ተቋማት እጅግ በጣም አነስተኛ ስለሆኑ በዚህ በድኅረ ምረቃ ፕሮግራሙ በቂ የሰው ኀይልን እና ምሁራንን በማፍራት እንደሌሎቹ አኅት አብያተ ክርስቲያናት ተጨማሪ የነገረ መለኮት ኮሌጆች ለመክፈት የሚያስችላትን አዲስ ዕድል ስለሚፈጥር፣

 

4ኛ. የድኅረ ምረቃ ፕሮግራሙ ከፍተኛ ጥናት እና ምርምር የሚደረግበት ስለሆነ ቤተ ክርስቲያናችን በሀገር ውስጥ እና በውጪ ሀገር አንድነቷ ተጠብቆ እንዲቆይ የሚያስችሏትን የመጻሕፍት ትርጉም ሥራዎች፣ የወንጌል አገልግሎትን ለማስፋፋት የምትከተላቸውን ስልቶችና ዘዴዎችን እንዲሁም በተለያዩ የቤተ ክርስቲያናችን ጉዳዮች የሚያጠነጥኑ ጥናቶችን እና ምርምሮችን በማድረግ ችግር ፈቺ እና የመፍትሔ አቅጣጫዎችን ጠቋሚ የሆኑ መረጃዎችን ለማግኘት ይህ ፕሮግራም እንደ ምንጭ ሆኖ ያገለግላል፡፡ ’’ በማለት ተናግረዋል፡፡

 

ከምክትል አካዳሚክ ዲኑ ሪፖርት ለመረዳት እንደተቻለው ኮሌጁ በ2005 ዓ.ም. የትምህርት ዘመን ለመጀመሪያ ጊዜ በመደበኛው መርሐ 4 (1)ግብር 33 ደቀ መዛሙርትን ተቀብሎ የመማር ማስተማሩን ሂደት ጀምሯል፡፡

 

በመርሐ ግብሩ ማጠናቀቂያ ላይ ብፁዕ አቡነ ናትናኤል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክና የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የሁለተኛ ዲግሪ የማስትሬት መርሐ ግብሩ  መጀመሩን በይፋ አብስረዋል፡፡

pop twadros election

የግብጽ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን 118ኛውን ፓትርያርክ መረጠች

ጥቅምት 26 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

የግብጽ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ለ40 ዓመታት ቤተ ክርስቲያኗን ሲመሩ የነበሩትንና በቅርቡ ያረፉትን ፓትርያርክ ብፁዕ አቡነ ሺኖዳ ሣልሳዊን ለመተካት 118ኛውን ፓትርያርክ እሑድ ጥቅምት 25 ቀን 2005 ዓ.ም. በታላቅ ሥነ ሥርዓት መረጠች፡፡

pop twadros electionበካይሮ አባሲያ ቅዱስ ማርቆስ ካቴድራል በተደረገው የእጣ አወጣጥ ሥነ ሥርዓት በእጩነት ከቀረቡት 3ቱ አባቶች መካከል አንዱን በፓትርያርክነት ለመሾም ዓይኑን በጨርቅ የተሸፈነ ሕፃን እጣውን እንዲያወጣ በማድረግ ብፁዕ አቡነ ታዋድሮስ / ቴዎድሮስ/ የግብጽ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ሆነው ተመርጠዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ታዋድሮስ በ1952 እ.ኤ.አ የተወለዱ ሲሆን በፋርማሲ ሳይንስ ከአሌክሳንደሪያ ዩኒቨርስቲ ተመርቀዋል፡፡ከ1997 pop twadrosእ.ኤ.አ ጀምሮ በጵጵስና ተሹመው የግብጽ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን በማገልገል ላይ ነበሩ፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በቅዱስ ሲኖዶስ ፈቃድ አምስት ጳጳሳትን ያቀፈ ልዑክ ወደ ግብጽ በመላክ በምርጫው ላይ ተሳትፈው መመለሳቸው ይታወሳል፡፡

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በጎቿን ይዛ እንድትዘልቅ …

ጥቅምት 26 ቀን 2005 ዓ.ም.


በየዓመቱ በጥምቀት ወር በቅድስት ቤተ ክርስቲያን የአስተዳደርና ዘርፈ ብዙ አገልግሎት ላይ የሚመክረው አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ለሠላሳ አንደኛ ጊዜ ተካሂዷል፡፡ በዚህ ጉባኤ ላይ የእናት ቤተ ክርስቲያናቸውን የአገልግሎት ጥሪ የተቀበሉ ምሁራን ልጆቿ፤ በልዩ ልዩ ርእሰ ጉዳዮች ላይ ያተኮሩ ጥናት ጽሑፎቻቸውን አቅርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡ በእንደዚህ ዓይነቱ ታላቅ ጉባኤ ላይ፤ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሁለንታዊ አገልግሎት መቃናት የሚበጁ፣ በየሙያ ዘርፉ ዕውቀትና ልምድ ባካበቱ ምሁራን ልጆቿ የሚቀርቡ የጥናት ጽሑፎችና የሚካሄዱ ውይይቶች፤ እናት ቤተ ክርስቲያን ትውልዱን ይዛ ዘመኑን እየዋጀች ጸንታ እንድትቀጥል በማድረግ ረገድ ጠቀሜታቸው የጎላ ነው፡፡

 

በቅድስት ቤተ ክርስቲያን የአገልግሎት ዘርፎች የተቀላጠፈና ዘመናዊ የአስተዳደር መዋቅርና አሠራር እንዲኖር ማድረግ ወቅቱም ሆነ ትውልዱ የሚጠይቀው ጉዳይ ነው፡፡ በዕቅድ ላይ የተመሠረተ በሪፖርትና ትክክለኛ ክትትል ባልተለየው ግምገማ የተደገፈ፣ ሓላፊነትና ተጠያቂነት ያለበት ማእከላዊ የፋይናንስ አስተዳ ደር ሥርዐት እንዲሰፍን ተጨባጭ ጥረት ያስፈልጋል፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቷ መንፈሳዊ ፍርድ ቤቷ ተጠናክሮ አስተዳደሯ፣ ሥርዐተ ከህነቷም ሆነ ሁለንተናዊ አገልግሎቷን የሚመለከቱ እንዲሁም የምእመናን መንፈሳዊ ጉዳ ዮች የሚዳኙበት አስተምህሮና ቀኖናዋን የጠበቀ መንፈሳዊ የፍትሕ ሥርዓት ተግባራዊ እንዲሆን ማድረግ ችላ የሚባልበት ወቅት አይደለም፡፡

 

ከሐዋርያዊ ተልእኮዋ ባሻገር በማኅበራዊ አገልግሎቷም የበለጠ እንድትሠራ፤ በልማት ሥራ እንድትበለጽግ፣ ገዳማቷና አድባራቷ በገቢ ራሳቸውን ችለው ከልመና እንዲላቀቁ በማድረግ ረገድ ከፍተኛ ሥራ ይጠበቅባታል፡፡ በእነዚህ ሁሉ መስኮች ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ምሁራን ልጆቿን በማሳተፍ በጥናትና ምርምር የተደገፈ ውጤታማ ሥራ ለመሥራት ቀዳሚ ትኩረት መስጠት እንዲሁም ሁኔታዎችን ማመቻቸትና የበለጠ ጥረት ማድረግ አለባት፡፡

 

አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ያለው ታላቅ መድረክ፤ በተራዘመ ሪፖርትና በተደጋገመ መልእክት የሚባክነው ጊዜ፤ በዓመት አንድ ጊዜ ከሚገኘው ጉባኤ ለቤተ ክርስቲያን የሚበጅ አሳብ፣ ዕቅድና መፍትሔ የሚቀርብበትን ምቹ ሁኔታ በማሳጣት ያለጥቅም እንዲያልፍ ያደርጋል፡፡ ለተሻለ አሠራርና ለበለጠ ውጤት የሚያበቃ የውይይት መድረክ የሚሆንበትን ዕድል ይነፍጋል፡፡

 

ስለዚህ እንዲህ ዓይነቶቹን ክፍተቶች በመገንዘብ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሁለን ተናዊ አገልግሎት የሚበጅ የጥናት ጽሑ ፎች እንዲቀርቡ ሐሳብ በመስጠት፣ ዕቅድ በማውጣት፣ ጊዜ፣ በጀትና የሰው ኀይል መድቦ ውይይቱ እንዲካሄድ የተደረገው ጥረትና የተከናወነው ሥራ የሚመሰገን ሲሆን ወደፊትም በተሻለ ሁኔታ ሊቀጥል የሚገባው ተግባር ነው፡፡

 

የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ጥሪ ተቀብለው እውቀታቸውንና ሙያዊ ልምዳቸውን ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት በሚበጅ ተግባር ላይ ለማበርከት በቀናነት የተሳተፉት ምሁራን ልጆቿ የሚመሰገኑ ናቸው፡፡ አገልግሎታቸው ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ ተልእኮ መቃናት፣ በዘመናዊ አሠራር በተደራጀ አስተዳደራዊ መዋቅር ዘርፈ ብዙ አገልግሎቷ የተሳካ አፈጻጸም እንዲኖረውና በልማት እንድትበለጽግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያበረክታል፡፡ እንዲህ ዓይነቱ አገልግሎት በልዩ ልዩ የሥራ መስኮችና ቦታዎች የተሰማሩት ምሁራን ልጆቿ በየተሰጣቸው ጸጋና ሞያ ለቤተ ክርስቲያን የሚጠበቅባቸውን አገልግሎት እንዲያበረክቱ በማነሣሣት ረገድ በአርአያነት የሚጠቀስ ነው፡፡

 

በየደረጃው ያሉት የቤተ ክህነቱ መዋቅርና አካላት ይህንኑ በጎ ልምድ መነሻ በማድረግ፤ በተለያየ ሙያና የሥራ መስክ የተሰማሩ ምሁራን በቤተ ክርስቲያን ልጅነታቸው ድርሻቸውን እንዲያበረክቱ በራቸውን ክፍት ማድረግና የአገልግሎት መድረኮችን ማመቻቸት እንደሚጠበቅባቸው ያመላክታል፡፡

 

በሠላሳ አንደኛው አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ላይ ከቀረቡት ጽሑፎች መካከል፤ ለምሳሌ “የዘመናችንን ትወልድ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ለማብቃት የአባቶች ሚና” በሚል ርእስ የቀረበው ጽሑፍም ከላይ ያነሣና ቸውን ነጥቦች በአጽንዖት የጠቆመ ነው፡፡

 

በጥናት ወረቀቱ እንደተጠቀሰው፤ የሕዝብ ብዛት እየጨመረ በመምጣቱ ምክንያት ጎልቶ አይታይ ይሆናል እንጂ በየጊዜው ሃይማኖታቸውን የሚተው፣ ከቤተ ክርስቲያናቸው የሚኮበልሉ ምእመናን ቁጥር ቀላል አይደለም፡፡ ምእመናንን ወደ ውጪ የሚገፉ በርካታ ውስጣዊና ውጫዊ ምክንያቶች አሉ፡፡ ከእነዚህም ምክንያቶች አንዱና ዋነኛው ከቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ጋር የሚያያዝ ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎቶች ይበልጥ እየተሻሻሉ ዘመኑን መዋጀት ካልቻሉ ውጤቱ ያማረ አይሆንም፡፡ ለዚህም ነው የዛሬውን ትውልድ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ብቁ እንዲሆን ማድረግ ወሳኝ ጉዳይ የሚሆነው በማለት የቀረበው ሐሳብ ትኩረት ሊሰጠው የሚገባ ነው፡፡

 

ምናልባትም በታላላቅ ከተሞች ባሉ ገዳማትና አድባራት የሚታየው እንቅስቃሴ፤ በወርና በዓመት የንግሥ ወይም ዐበይት በዓላት የሚታየው የሕዝበ ክርስቲያኑ ብዛትና ድምቀት በየገጠሩና በየበረሐው ያለውን አገልግሎት እንቅስቃሴና የምእመናኑን መጠን የሚያሳይ ነው የሚል የተሳሳተ ግምት ካለ፤ ገሐድ እውነቱ ከተሳሳተው ግምት የተለየ መሆኑን መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡

 

ስለዚህ ትውልዱን በቤተ ክርስቲያን እቅፍ ሰብስቦ ለአገልግሎት በማብቃት የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሁለንተናዊ አገልግሎት ዘመኑን በዋጀ ውጤታማ አሠራር በተሳካ ሁኔታ ማፋጠን የወቅቱ ጥያቄ ነው፡፡ አሁን ባለው ዘመንና ትውልድ ደግሞ ሉላዊነትን (Globalization) መሠረትና ጉልበት ያደረገ ሥልጣኔ የተስፋፋበት፣ ዘመናዊነት የነገሠበት እንደመሆኑ፤ በዓለማችን የሚከሠቱ ተጨባጭ ሁኔታዎች በአንድም ሆነ በሌላ መንገድ አሉታዊም ሆነ አዎንታዊ ተጽዕኖ አቸው እያየለ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሕልውናና አገልግሎት ፈተናዎች እየሆኑ ይታያል፡፡

 

ከዘመኑ የኑሮ ሁኔታ፣ የሥልጣኔ ውጤቶች፣ በተዛባ የዘመናዊነት ግንዛቤ የሚከሠቱት ዓለም አቀፋዊ ተጽዕኖዎች በተለይ በመንፈሳዊ ሕይወቱ የሚያሳድሩበትን ጫና እንዲቋቋም አድርጎ ለጥያቄዎቹ ምላሽ በመስጠት ትውልዱን ይዞ ለመቀጠል ቅድስት ቤተ ክርስቲያን አፋጣኝ መፍትሔ ልትሰጠው የሚገባ ተግባር ነው፡፡

 

ስለዚህ በየአጥቢያው የስብከተ ወንጌል አገልግሎትን ማስፋፋት፣ ጉባዔያትን ማጠናከር፤ ለሰንበት ትምህርት ቤቶች ልዩ ትኩረት ሰጥቶ በቅርበት ዕለት ዕለት መከታተል፣ መምህራነ ወንጌል መመደብ፣ ቅዱሳት መጻሕፍትን ማሟላት፣ ሰንበት ትምህርት ቤቶችን በማጠናከርና በማስፋፋት አገልግሎታቸውም በበለጠ ጥረት የተሻለ ውጤት እንዲኖረው በማድረግ ረገድ ከፍተኛ ሥራ ይጠበቃል፡፡

 

ከፍተኛ የመንፈሳዊ ትምህርት ተቋማቱን በተሟላ አደረጃጀትና ዘመናዊ አሠራር እያጠናከሩ ማስፋፋት እውነተኛ የቤተ ክርስቲያን ልጆች በቀና ዓላማ ገብተው በቂ ዕውቀት ቀስመው ለአገልግሎት እንዲዘጋጁ ያስችላቸዋል፡፡ ሌሎችም የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ መንገዶችን የቴክኖሎጂውን እድገትና ዕድል በመጠቀም፤ በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ በመላው ዓለም በየቦታው ላይ ለምእመናን፤ በመገናኛ ብዙኃን ቃለ እግዚአብሔርን ማድረስ የግድ ይላል፡፡

 

አብነት ትምህርት ቤቶቻችን በብዙ ችግሮች ተተብትበው መምህራኑም ሆኑ ደቀ መዛሙርቱ ፈተና ላይ ወድቀዋል፡፡ የትምህርት አሰጣጥ ዘዴው ጊዜን፣ ቁሳዊ ሃብትን፣ ወቅትንና ሌሎችም አካባቢያዊ ሁኔታዎችን ባገናዘበ ሁኔታ ተመቻችቶ ባለመካሄዱ በቀጣይነቱ ላይ የተጋረጠ ትልቅ ፈተና ነው፡፡ ችግሮቹን አዝሎ ያንዣበበው አደጋ ከቀጠለ የካህናትና ሊቃውንት አገልጋዮቿ ምንጭ እየተዳከመ የነገይቱ ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ስኬትም አጠያያቂ መሆኑን ከወዲሁ ማሰብ፤ አፋጣኝ መፍትሔ መፈለግና በተግባር ማረጋገጥ አስፈላጊ ነው፡፡ ሊቃውንቱ እንዲያስተምሩ፣ የተካበተ ዕውቀታቸው ለምእመናን እንዲደርስ መርሐ ግብር ማዘጋጀት፣ መድረኮችን ማመቻቸትና እንዲሳተፉ ማድረግ ይገባል፡፡ ከዚህም በላይ ሰፊ የዕውቀት ሀብታቸው፣ ከመንፈሳዊው አገልግሎትና ሕይወታቸው ልምድ ጋር ለትውልድ እንዲተላለፍ ምእመናን እንዲጠቀሙበት ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እንዲጽፉ ማበረታታት፣ የሚያስፈልጋቸውን ማገዝ ማሳሰብ ትኩረት ሊሰጠው የሚገባ ጉዳይ ነው፡፡

 

የቅድስት ቤተ ክርስቲያን አባቶችና አገልጋዮች ትውልዱን ከማስተማር ጎን ለጎን የዕለት ተዕለት ክትትልና መንፈሳዊ ጥበቃ ማድረግ እንዳለባቸው ዋነኛ የአባትነት ሓላፊነታቸው እንደሆነ የታወቀ ነው፡፡ ከዚሁ ጋር በሕይወታቸው መልካም አርአያ በመሆን ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት መትጋትና ሃይማኖታዊ ሓላፊነታቸውን በሚገባ መወጣት አለባቸው፡፡

 

በአጠቃላይ በጎቹን በቃለ እግዚአብሔርና በመንፈሳዊ ሕይወት ጠብቆ በእናት ቤተ ክርስቲያን እቅፍ እንዲዘልቅ፤ በቀና መንፈስ በአገልግሎት እንዲሳተፍ ማስቻል፣ በፍቅርና በመልካም የአባትነት አርአያ መቅረብ፣ መከታተል ትኩረት ሊሰጠው የሚገባ ቀዳሚ ሥራ ነው እንላለን፡፡

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

  • ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 20ኛ ዓመት ቁጥር 4 2005 ዓ.ም.

በማኅበረ ቅዱሳን የአርባ ምንጭ ማእከል 14ኛውን ጠቅላላ ጉባኤ እየተካሄደ ነው

ጥቅምት 24 ቀን 2005 ዓ.ም.

ከአርባ ምንጭ ማዕከል


በማኅበረ ቅዱሳን የአርባ ምንጭ ማእከል ከጥቅምት 23-25ቀን 2005 ዓ.ም 14ኛውን ጠቅላላ ጉባኤ በመካሔድ ላይ ነው ፡፡ በመክፈቻ መርሐ ግብሩ ላይ ከሀገረ ስብከት የመምሪያ ሓላፊዎች፣ በአርባ ምንጭ ከተማ የሚገኙ የአድባራት አስተዳዳሪዎች እና ሰበካ ጉባኤያት፣ የሰንበት ትምህርት ቤት ተወካዮች ፤  የ16 ወረዳ ማእከላት እና 3 ግንኙነት ጣቢያዎች ፤ የ10 ግቢ ጉባኤያት ተወካዮች እና ጥሪ የተደረገላቸው ተጋባዥ እንግዶች ተገኝተዋል፡፡

 

ለሁለት ቀናት በሚቆየው ጉባኤ የማእከሉ የ2004 የሥራ ክንውን ሪፖርትና የ2005 ዕቅድ ቀርቦ ውይይት የሚያካሂድ ሲሆን በተጨማሪም በተለያዩ አጀንዳዎች ዙሪያ ውይይት ያደርጋል፡፡

 

  • በተለይም ትኩረት የሚደረግባቸው አጀንዳዎች
  1. የአራት ዓመቱ ስትራቴጂክ እቅድ አፈፃፀም
  2. የወረዳ ማእከላት እንቅስቃሴ የሚያሳይ የዳሰሳ ጥናት
  3. የአብነት ትምህርት ቤቶችና የአብያተ ክርስትያናት የልማት እንቅስቃሴዎችን ማሳየት
  4. ግቢ ጉባኤያትን ለሐዋርያዊ አገልግሎት ማብቃት

በሚሉ ርዕሰ ጉዳዮች ዙሪያ ውይይት በማድረግ ውሳኔዎችን ያሳልፋል ተብሎ እንደሚጠበቅ የማእከሉ ሰብሳቢ አቶ ገናነው ፍሰሐ ገልጸዋል፡፡

የአዲስ አበባ ማእከል 18ኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤ ተካሄደ፡፡

ጥቅምት 22 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ


የአዲስ አበባ ማእከል 18ኛ ጠቅላላ ጉባኤ ከጥቅምት 17-18 ቀን 2005 ዓ.ም. በጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ ለሁለት ቀናት ተካሄደ፡፡

 

መርሐ ግብሩ በመንበረ ልዑል ቅዱስ ማርቆስ ቤተ ክርስቲያን ልዑካን ጸሎተ ወንጌል በማድረስ በብፁዕ አቡነ ዮሴፍ የባሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ቡራኬና ጸሎት ተጀምሯል፡፡

 

በአዲስ አበባ ማእከል ሰብሳቢ በዲያቆን አንዱ ዓለም ኀይሉ የመክፈቻ ንግግር ጉባኤው የቀጠለ ሲሆን በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስት ማርያም ገዳም የፈለገ ሕይወት ሰንበት ትምህርት ቤት አባላት ያሬዳዊ ዝማሬ በማቅረብ የወንጌል ትምህርት በቀሲስ ፋሲል ታደሰ ተሰጥቷል፡፡

 

በተያዘለት የጊዜ መርሐ ግብር መሠረት የ2004 ዓ.ም. ዓመታዊ እቅድ ክንውን አፈጻጸምና የ2003 ዓ.ም. ኦዲትና ኢንስፔክሽን ሪፖርት ቀርቧል፡፡

 

በ2004 ዓ.ም. ዓመታዊ እቅድ ክንውን በተመለከተ ማእከሉ የማኅበረ ቅዱሳንን የማስፈጸም አቅም ከማጎልበት አንጻር፣ ግቢ ጉባኤያትን ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ማብቃት፣ ስብከተ ወንጌልን ማስፋፋት፣ አጽራረ ቤተ ክርስቲያን በቤተ ክርስቲያን ላይ የሚያደርሱትን ጥቃት መግታት፣ የቅዱሳት መካናት፣ የአብነት ትምህርት ቤቶችንና ሰንበት ትምህርት ቤቶችን አቅም ከማጠናከር አንጻር የቤተ ክርስቲያንን እና የምእመናንን ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተሳትፎ ማሳደግ፣ ጠንካራ የመረጃ ሥርዓት እና ሚዲያ መዘርጋት በሚሉ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ የታቀዱትን በማስፈጸም ረገድ የተከናወኑትን በዝርዝር ቀርበዋል፡፡ በተጨማሪም ደጋፊ ተግባራት ተብለው በእቅድ የተያዘለትን የጽ/ቤት፣ የአባላት አገልግሎት ማስተባበሪያ ክፍል፣ ግቢ ጉባኤ አገልግሎት ማስተባበሪያ ክፍል፣ ትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ክፍል፣ የልማት ተቋማት አስተዳደር፣ ማኅበራዊ አገልግሎትና ልማት ክፍል ሂሣብና ንብረት ክፍል፣ የእቅድ ዝግጅትና ክትትል ክፍሎችን የወረዳ ማእከላት አጠቃላይ አፈጸጸም የተከናወኑትን በመቶኛ በማስላት ቀርበዋል፡፡

 

በአገልግሎት ላይ በዓመቱ ውስጥ ያጋጠሙ ችግሮች በሪፓርቱ የተዳሰሱ ሲሆን በተለይም ከሀገረ ስብከት ጋር ከተወሰኑ የአገልግሎት ግንኙነት በዘለለ ጠንካራ ግንኙነት ለመፍጠር ምላሽ ማጣት፣ ልምድ ያላቸው የግቢ ጉባኤያትን በሚገባ ሊመሩ ሊቆጣጠሩ የሚችሉ የግቢ ጉባኤያትን ሙሉ በሙሉ የሚያስተባብሩ አስተባባሪዎች ያለማግኘት ወርኀዊ አስተዋጽኦ በማሰባሰብ ሂደት ውስጥ የክፍሎች ተሳትፎ ማነስ ይጠቀሳሉ፡፡

 

ትኩረት ከሚሹ ጉዳዮች መካከልም ከሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት ጋር ግንኙነት ማጠናከር፣ የሠራተኛ ጉባኤትን አያያዝና ቀጣይ ሂደት፣ ከቁጥር ይልቅ ጥራት ላይ ትኩረት ማድረግ እንደሚገባ ተገልጿል፡፡

 

በቀረበው ሪፖርት ላይ መነሻ በማድረግ ከተሳታፊዎች ለቀረቡ ጥያቄዎች በሚመለከታቸው የክፍሉ ሓላፊዎች ምላሽ ተሰጥቷቸዋል፡፡

 

ከሰዓት በኋላ በተደረገው መርሐ ግብር ላይ በማኅበረ ቅዱሳን የወረዳ ማእከላት የአገልግሎት እና የወደፊት አቅጣጫ ዳሰሳዊ ጥናት ለጠቅላላ ጉባኤው ቀርቧል፡፡ በጥናቱ ላይ ከተካተቱት ዋና ዋና ጉዳዮች መካከል የአባላት ተሳትፎ የወረዳ ማእከላት እንቅስቃሴ፣ የአጥቢያ ቤተ ክርስቲያናት ከማኅበረ ቅዱሳን ወረዳ ማእከላት ጋር ያለው ክፍተት የወረዳ ማእከላት ከአዲስ አበባ ማእከል ጋር ያላቸው ግንኙነት በጥናቱ የተዳሰሱ ሲሆን ሊወሰዱ የሚገባቸው መፍትሔዎች ከአባላት፣ ከወረዳ ማእከላት፣ ከሰንበት ትምህርት ቤቶች ከስብከተ ወንጌል ከሰንበት ትምህርት ቤቶች ኅብረት የሚጠበቁትን በዝርዝር አቅርበዋል፡፡ በመጨረሻም በቀረበው ጥናት ላይ ውይይት ተደርጓል፡፡

 

በማግስቱ እሑድ ጥቅምት 18 ቀን 2004 ዓ.ም. በተካሄደው የጠቅላላ ጉባኤ ውሎ ሥልታዊ አገልግሎት ለቤተ ክርስቲያን ሁለንተናዊ እድገት ከማእከላት አቅም አንጻር በሚል ርዕስ ጥናት የቀረበ ሲሆን በጥናቱ ላይ ውይይት ተካሂዶበታል፡፡ የወንጌል ትምህርት፣ የ2005 ዓ.ም. የሥራና የበጀት እቅድ፣ በእቅዱ ላይ የተካሄደ ውይይትና በማእከሉ መዘምራን ያሬዳዊ ዝማሬ ቀርበዋል፡፡ በመጨረሻም የዋናው ማእከል መልእክት በማድመጥ መርሐ ግብሩ በጸሎት ተጠናቋል፡፡

የጥቅምቱ ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ተጠናቀቀ

ጥቅምት 21 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ

 

በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ 5 ቁጥር 164 በተደነገገው መሠረት ጥቅምት 11 ቀን 2005 ዓ.ም. ጀምሮ ለአሥር ቀናት ያህል በ17 አጀንዳዎች ላይ ሲነጋገር የሰነበተው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ አስፈላጊ ናቸው ያላቸውን ውሳኔዎችን በማስተላለፍ ዛሬ ከቀትር በፊት ተጠናቀቀ፡፡

 

ባለፈው ዓመት የተከናወነውን ሥራ ለመገምገምና የወደፊቱንም እቅድ ለመንደፍ እንዲችል ከየአህጉረ ስብከቱ ጽ/ቤቶች የቀረቡለትን ሪፓርቶች አዳምጦ አስፈላጊውን መመሪያ የሰጠው ቅዱስ ሲኖዶስ በሰሜን አሜሪካ ከሚገኙት አባቶች ጋር የተጀመረው የእርቀ ሰላም ድርድር ተጠናክሮ ይቀጥል ዘንድ ውሳኔ አሳልፏል፡፡

 

ስድስተኛውን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ምርጫ አስመልክቶ እስከ ኅዳር 30 ቀን 2005 ዓ.ም. ድረስ የፓትርያርክ ምርጫ ሕግ እንዲዘጋጅ ኮሚቴ የተቋቋመ ሲሆን፤ ኅዳር 30 ቀን 2005 ዓ.ም በሚደረገው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ስብሰባ ሕጉ ተመርምሮ እንዲጸድቅና የምርጫ ሂደቱ እንዲቀጥል ከስምምነት ተደርሷል፡፡

 

የአዲስ አበባን ሀገረ ስብከትን አስመልክቶ ለመንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት አፈጻጸም ያመች ዘንድ በምሥራቅ፣ በምዕራብ፣ በሰሜንና በደቡብ በአራት አህጉረ ስብከት እንዲዋቀር፤ ለእያንዳንዱ ሀገረ ስብከት ከብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ጀምሮ ሥራ አስኪያጆችና ሠራተኞች እንዲመደቡ ተወስኗል፡፡

 

በብፁዕ አቡነ ናትናኤል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክ የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ አማካኝነት የተነበበው የቅዱስ ሲኖዶስ መግለጫ፤ የውጭ ግንኙነትን በተመለከተ በአፍሪካ፣ በአውሮፓ፣ በአሜሪካና በሌሎችም አህጉር አገናኝ ዴስክ እንዲቋቋም የቤተ ክርስቲያኒቱ እንቅስቃሴ የሚዳስስ በእንግዚዝኛና በአማርኛ ቋንቋ የሚዘጋጅ ወርኅዊ መጽሔት እንዲኖር፤ መምሪያውንም የበለጠ ለማጠናከር ይቻል ዘንድ በሰው ኀይልና በበጀት እንዲደገፍ ውሳኔ ተላልፏል፤ በሌላ በኩል የአብነት ትምህርት ቤቶችን ገዳማትንና የካህናት ማሠልጠኛዎችን በበጀት አጠናክሮ በበለጠ እንዲሠሩ ለማድረግ የ10 ሚሊየን ብር በጀት እንዳጸደቀ አመልክቷል፡፡

 

ከዚህ በተጨማሪ አንዳንድ “የስም መነኮሳት ነን” ባዮች የቤተ ክርስቲያኒቱን የምንኩስና ልብስ እየለበሱ ሕዝቡን በማትለልና ሃይማኖታችንን በማስነቀፍ ተግባር ተሰማርተው እንደሚገኙ ይታወቃል፤ ስለሆነም ሕዝበ ክርስቲያኑ ከእነዚህ ምግባረ ብልሹ ወገኖች ራሱን ነቅቶ እንዲከላከልና መንግሥትም የሕግ ከለላ እንዲሰጥ ቅዱስ ሲኖዶስ በአጽንኦተ ይጠይቃል፡፡” ብሏል፡፡

 

ከመግለጫው በኋላ ከጋዜጠኞች ለተነሡ ጥያቄዎች ምላሽ የሰጡት የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሓፊና የከፋ ሸካ ቤንች ማጂ ዞን አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ አቡነ ሕዝቅኤል የጳጳሳትን ንብረት አስመልክቶ፡- “በመሠረቱ ጳጳስ የእኔ፣ የግሌ የሚለው ሀብት ንብረት የለውም፡፡ ሊኖረውም አይገባም፡፡ ንብረቶቹ ሁሉ ምእመናን ናቸው፡፡ ምእመናን ሲባል ቤተ ክርስቲያኒቱን ማለት ነው፡፡ ከዚህ ውጪ ጎመን የሚዘራበት፣ ሽንኩርት የሚተክልበት የእርሻ ቦታ እንኳ የለውም” በማለት ተናግረዋል፡፡

 

የቅዱስ ሲኖዶስን መግለጫ ዝርዝር ዘገባ በቅርቡ እናቀርባለን፡፡

aa 001

ሊቀ ጉባኤ ኀይለ ማርያም ዐረፉ

ጥቅምት 20 ቀን 2005 ዓ.ም.

በቀሲስ ለማ በሱፍቃድ


aa 001ሊቀ ጉባዔ ኀይለ ማርያም ንጋቱ ከአባታቸው ከአቶ ንጋቱ ወልደ ሐዋርያትና ከእናታቸው ከወ/ሮ ደመዎዝ ወንድም አየሁ ጥር 12 ቀን 1969 ዓ.ም በሰሜን ሸዋ በሞረትና ጅሩ ወረዳ ልዩ ስሟ ሽነት ቁስቋም በምትባል መንደር ተወለዱ፡፡ ገና በሕፃን ዕድሜያቸው ወደ ታላቁ ገዳም ወደ ደብረ ጽጌ ማርያም በመሄድ ለአጎታቸው ለአባ ፀጋ ወልደ ሐዋርያ በአደራነት ተስጥተው የቅድስት ቤተ ክርስቲያናቸውን ትምህርት ሀ ብለው ንባብ ከአባ ሀብተ ማርያም በሚገባ ካጠናቀቁ በኋላ እዛው ገዳሙ ውስጥ ከሚገኙት ከመምህር አፈወርቅ የቃል ትምህርትና ጾም ምዕራፍ በሚገባ ተማሩ እንዲሁም ከታላቁ ሊቅ ከየኔታ ጽጌ ጾመ ድጓና ድጓ ተምርው በመምህርነት ተመርቀዋል፡፡ ቀጥሎም አቋቋምና ዝማሬ መዋሲእት ከየኔታ መስፍን አበበ በሚገባ ተምርው ተመርቀዋል፡፡ ይህን ሁሉ ትምህርት ተምሬያለሁ በቃኝ ሳይሉ ተጨማሪ ቃለ እግዚአብሔር ፍለጋ በ1984 ዓ.ም ወደ አዲስ አበባ በመምጣት በታዕካ ነገሥት በዓታ ለማርያም ገዳም የካህናት ማሠልጠኛ በመግባት የእውቀት አድማሳቸውን በማስፋት የተክሌ አቋቋምን በመማር በመምህርነት ተመርቀዋል፡፡

 

ሊቀ ጉባዔ ኀይለ ማርይም ንጋቱ በ1986ዓ.ም በገዳሙ ውስጥ በዲቁና እንዲያገለግሉ ተቀጥረዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በነበራቸው መንፈሳዊ ትጋት የተነሣ በመሪ ጌትነት፣ በሊቀ አርድእትነት፣ በሊቀ ጉባኤነት፣ የትምህርት ቤቱ ተቆጣጣሪና ዋና ጸሐፊ በመሆን ከሃያ ዓመታት ላላነሱ ጊዜያት በልዩ ልዩ የሓላፊነት ቦታዎች በቅንንትና በታማኝነት አገልግለዋል፡፡ ሊቀ ጉባኤ ኀይለ ማርያም  በአስኳላው ትምህርታቸው እስከ አሥራ ሁለተኛ ክፍል ድረስ ተከታትለዋል፡፡

 

ሊቀ ጉባኤ ኀይለ ማርያም ባደረባቸው ሕመም ምክንያት በሕክምናና በጠበል ሲረዱ ቆይተው በተወለዱ በ36 ዓመታቸው ጥቅምት 6 ቀን 2005 ዓ.ም ከዚህች ዓለም በሞተ ሥጋ ተለይተዋል፡፡ ሥርዓተ ቀብራቸውም ጥቅምት 7 ቀን 2005 ዓ.ም በደብረ ሊባኖስ ገዳም ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና ወዳጅ ዘመዶቻቸው በተገኙበት ተፈጽሟል፡፡ ሊቀ ጉባኤ ኀይለ ማርያም ባለ ትዳርና የአንድ ወንድ ልጅ አባት ነበሩ፡፡

ስርጭቱን ለማስቀጠል ጥረቶች እየተደረጉ መሆኑ ተገለጠ፡፡

ጥቅምት 19 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ


በኢ.ቢ.ኤስ ቴሌቪዥን አማካኝነት ከጥቅምት 4 ቀን 2005 ዓ.ም. ጀምሮ ይሠራጫል በሚል በምእመናን ዘንድ በጉጉት ሲጠበቅ የነበረው የማኅበሩ የቴሌቭዥን መርሐ ግብር የኢ.ቢ.ኤስ ጣቢያ ከጥቂት ጊዜያት ወዲህ ሙሉ ሥርጭቱ በመቋረጡ የተነሣ በታሰበው ጊዜ ለመጀመር አልተቻለም፡፡ ሆኖም የኢ.ቢ.ኤስ ሓላፊዎች በገለጹት መሠረት ጣቢያው እንደገና ሥርጨቱን ለማስጀመር ከፍተኛ እንቅስቃሴ እየተደረገ ሲሆን ችግሩ እንደተቀረፈም የማኅበሩ ቴሌቪዥን  የሚጀምር መሆኑን አስተባባሪው ዲ/ን ሄኖክ ኃይሌ ለዝግጅት ክፍላችን አስታውቀዋል፡፡

Aratu 2 (2)

፬ቱ ሆሄያት

ጥቅምት 19 ቀን 2005 ዓ.ም/

በዲ/ን ኅሩይ ባየ

Aratu 2 (2)የመስቀል ደመራ በናፍቆት የምንጠብቀው በዓል ነው፡፡ ከልሂቅ እስከ ደቂቅ በበዓሉ ይታደማል፤ በመዝሙር አምላኩን ያመሰግናል፡፡ ዛሬም እንደጥንቱ በያዝነው ዓመት በደመቀ መልኩ ተከብሯል፡፡ የሰንበት ት/ቤት ወጣቶችም የተለያዩ መንፈሳዊ ተውኔቶችን በማቅረብ መልእክት አስተላልፈዋል፡፡

 

የደቡብ ክፍለ ከተማ ሰንበት ት/ቤት ወጣቶች አራቱ ሆሄያት ተከብረውና ተጠብቀው መቀጠል እንዳለባቸው አስገንዝበዋል፡፡ የሆሄያቱ ጉዳይ ለበርካታ ጊዜያት ሲያከራክር የኖረ በመሆኑ ትኩረታችንን በዚሁ አድርገናል፡፡

 

አንድ ሀገር የራሱ የሆነ ቋንቋ፣ ባህል፣ እምነት፣ ታሪክ፣ ትውፊት፣ ሥነ ጽሑፍና ሥነ ቃል ይኖረዋል፡፡ ማኅበረሰቡም አኗኗሩን፣ የሚኖርበትንም አካባቢ የሚገልጥበት የአፍና የጽሑፍ ጥበቦችን እንደሚጠቅም ይታወቃል፡፡ ቃላዊና ቁሳዊ ተብሎ የሚከፈለው የሥነ ባህል ኀልዮት ራሱን ችሎ የሚተገበር ርዕዮተ ዓለም (ፍልስፍና) አለው፡፡

 

ኢትዮጵያ ከምትታወቅባቸው ዐበይት ሀብቶቿ ውስጥ አንዱ የራሷ የሆነ ፊደልና ቋንቋ እየተጠቀመች ለትውልድ ስታስተምር መኖሯ ነው፡፡ ለዚህም የፊደል፣ የቋንቋ ዕድገትና ሥልጣኔ ከፍተኛውን ድርሻ የምትይዘውና በር ከፋቿ የኢትዮጵያ  ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ ቤተ ክርስቲያን ዛሬም እንደ ጥንቱ የሆሄያቱ ታሪክ እንዳይረሳ መልክአቸው እንዳይጠፉ ለትውልዱ ታስተምራለች፡፡ ስለሆነም በዘንድሮው የመስቀል በዓል በመስቀል ዐደባባይ አራቱ ሆሄያት እንዳይረሱ ትኩረት እንደሚያሻቸው ጥሪ ቀርቧል፡፡

 

ሆሄ የሚለውን ቃል ፊደል ተብሎ ሲነገር እንሰማለን፤ በጽሑፍም እናነባለን፡፡ ፊደልን ፈደለ ጻፈ ካለው የግእዝ ግስ አውጥተን ጽሑፍ የሚለውን ትርጉም እናገኛለን፡፡ በሌላ አተረጓጐም ፊደል የሚለው ግስ ጠብቆ ሲነበብ ፈጠረ የሚለውን ትርጉም ያስገኛል፡፡ ፊደል ፈጣሪ /መፍጠሪያ/ መባሉም ቃላትን ስለሚያስገኝ ነው፡፡ አባቶቻችን “ዘእንበለ ፊደል ኢይትነገር ወንጌል.. ያለፊደል ወንጌል አትተረጐምም” ማለታቸው ለመጻፍም ሆነ ለማንበብ፤ ለመተርጐምም ሆነ ለማመስጠር ፊደላት ጉልሕ ድርሻ እንዳላቸው ሲያመለክቱ ነው፡፡

 

ፊደል መጽሔተ /መስተዋት/ አእምሮ ነው፤ በመስተዋት የፊትን ጉድፍ ማየትና ራስን መመልከት እንደሚቻለው ሁሉ፤ ልብ ማድረግን፥ ዕውቀትንና ጥበብን የሚገልጡ ፊደላት ስለሆኑ መጽሔተ አእምሮ ተብለዋል፡፡ ፊደል ነቅዐ ጥበብ ሊባልም ይችላል፡፡ የጥበብ መገኛ፣ መፍለቂያ፣ መመንጪያ ናቸውና፡፡ ፊደል መራሔ ዕውራን ማለት ነው፡፡ ዐይነ ስውር በበትር እንዲመራ ዕውቀት ለጠፋበት ልቡናው ለደነዘዘበት የዕውቀት ድካም ላለበት ሰው ፊደልን ቢቆጥር ቢያጠናና ቢያውቅ ካለማወቅ ዕውርነት ወደ ዕውቀት ብርሃንነት ስለሚመለስ ፊደላትን መራሔ ዕውራን እንላቸዋለን፡፡ ፊደል ጸያሔ ፍኖት ወይም መንገድ ጠራጊ ነው፡፡ ንባብን ተገንዝቦ ምስጢርን ለማደላደል ፊደል ጥቅም አለው፡፡

 

ሆሄ /ፊደል/ በቁሙ ከምናየው መልክዐ ገጽ አልፎ በውስጡ የያዘው ታሪካዊ፣ አመክንዮአዊና ምስጢራዊ መልእክቶች አሉት፡፡ በዚህ አጭር ጽሑፍ የሁሉንም ሆሄያት ስያሜያቸውንና ምስጢራቸውን ማየት አንችልም፡፡

 

የግእዝን ቋንቋ ፊደል በተመለከተ ብዙ አስተያየቶች ቢኖሩም በአንድ ነገር መስማማት ይቻላል፡፡ ሆሄ ወይም ፊደል በቁሙ ከምናየው መልክዐ ገጽ አልፎ በውስጡ የያዘው ታሪካዊ፣ አመክንዮአዊና ምስጢራዊ መልእክቶች አሉት፡፡ የፊደልን ጠቀሜታ የትመጣና ሚና አስረስ የኔሰው ‹‹የካም መታሰቢያ የኢትዮጵያ ፊደል መሠረትነት መታወቂያ›› በተሰኘው መጽሐፋቸው እንዳመለከቱት “ፊደል ሐውልት ነው፤ ሐውልትም ፊደል ነው፤ ፊደል መልክ ነው፤ መልክም ፊደል ነው፤ ፊደል አባት ነው፤ አባትም ፊደል ነው፤ ፊደል ልጅ ነው፣ ልጅም ፊደል ነው፤ ፊደል ወሰን ነው፡፡ ወሰንም ፊደል ነው፣ ፊደል ዓላማ ነው፣ ዓላማም ፊደል ነው፡፡

 

በወትሯዊ የጽሑፍ ተግባራችን የምንጠቀምባቸው ወደ አራት የሚደርሱ ሆሄያት አሉ፡፡ እነዚህ ፊደላት እነማን እንደሆኑ በቦታው እንገልጠዋለን፡፡ አራቱ ፊደላት በሥነ ድምፅ ትምህርት መካነ ፍጥረታቸው ተመሳሳይ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ልዩነታቸው በጽሑፍ ላይ ቢሆንም የመገኛቸው ቦታና የድምፃቸው ጠባይ ሊመሳሰል ይችላል፡፡ እነዚህ ሆሄያት በቃላት ውስጥ ሲገቡ የተለያየ የትርጉም ለውጥ የማምጣት ኀይል አላቸው፡፡ አራቱን ሆሄያት ጠንቅቀው የሚጽፉ ጸሐፍት ቢኖሩም ዕያወቁ በቸልተኝነት ሳያውቁ በስሕተት እጃቸው እንዳመጣ የሚጽፉ ደግሞ አያሌ ናቸው፡፡

 

ዶ/ር አምሳሉ አክሊሉ “የሆሄያት አጠቃቀም ችግር” በተባለው መጽሐፋቸው ሆሄያትን በአግባቡ መጠቀም የሚፈልጉና የማይፈልጉ ሰዎች ሦስት ምክንያቶችን እንደሚያቀርቡ አብራርተዋል፡፡ የመጀመሪያዎቹ ለፊደላችን ሥርዐትና ወግ ሊበጅላቸው ያስፈልጋል፡፡ በዘፈቀደ መጻፍ እንደግዴለሽነትና ሥርዓት አልበኝነት ያስቆጥራል፤ ያለሥርዐት የሚተገበር ማንኛውም የሰዎች ሕግ ጠቀሜታ የለውም የሚል ሐሳብ ያቀርባሉ፡፡ በኹለተኛው በኩል ያሉ ወገኖች ደግሞ እንደተለመደው ለእጃችን የቀረበውን ሆሄ ብንጠቀምበት ምን ችግር አለው ይላሉ፡፡ በሦስተኛው ወገን ያሉ ሰዎች ደግሞ ለጽሕፈታችን ሥርዐት ተሠርቶለት ከኹለት አንዱን ፊደል መርጦ መጠቀም ይበጃል ይላሉ፡፡ ከሦስቱም ምሁራዊ አመክንዮዎች መካከል የፊደላቱን የትመጣና ብያኔ ምሥጢራዊ ፍቺ ጠንቅቀው የሚተረጉሙ ሊቃውንት የመጀመሪያውን ሐሳብ ይደግፋሉ፤ ተገቢና ምክንያታዊ በመሆኑም ቤተ ክርሰቲያናችን ትቀበለዋለች፡፡

 

በግእዝ  ሆሄያት ከሀ-ፐ ድረስ ያሉት ፊደሎች ቁጥር26 ናቸው፡፡ ከእነዚህም አራቱ ሆሄያት ይገኙባቸዋል፡፡ እነዚህ ሆሄያት ከላይ እንደገለጥነው የራሳቸው የሆነ መጠሪያ ስም አላቸው፡፡ ስም ያለው አካል የተለያየ ጠባይና ማንነት ቢኖረው እንጂ ፍጹም አንድነት ሊኖረው አይችልም፡፡ አራቱ ሆሄያት ናቸው የምንላቸው፡-

  1. ሀ፣ ሐ፣ ኀ /ሃሌታው “ሀ”፣ ሐመሩ “ሐ”ና ብዙኀኑ “ኀ”

  2. ሠ፣ ሰ፣ /ንጉሡ “ሠ” ና እሳቱ “ሰ”

  3. አ፣ ዐ አልፋው “አ” ና “ዐይኑ “ዐ”

  4. ጸ፣ ፀ /ጸሎቱ “ጸ” ና ፀሐዩ “ፀ” ናቸው፡፡.

 

እነዚህን ሆሄያት እየቀላቀሉ መጻፍ የትርጉም ለውጥ የሚያመጡ ቃላትን እንደመፍጠር ነው፡፡ አንዱን ከሌላው እያቀላቀሉ መጻፍ ምን ያህል አሳፋሪ እንደሆነ አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ ‹‹መጽሐፈ ሰዋሰው ወግስ ወመዝገበ ቃላት ሐዲስ›› በተሰኘው መጽሐፋቸው ሲገልጡ፡-

“እንዳገኙ መጣፍ በድፍረት በመላ

የቋንቋ ደረመን የመጽሐፍ ቢስገላ

ንባብ የሚያሳክክ ምስጢር የሚቆምጥ

መልክዐ ትርጓሜ የሚለውጥ” ብለዋል

 

በዘመናዊ መንገድ በጽሑፍ ማሽን መጻፍ ከመጀመሩ በፊት ከሸምበቆ /መቃ/ ብዕር ተቀርጾ ከዕፀዋት ቀለም ተዘጋጅቶ ከእንስሳት ቆዳ ብራና ተዳምጦ በእጅ ጽሑፍ ይጻፍ ነበር፡፡ ጸሐፊውም ቁም ጸሐፊ ተብሎ ሲጠራ ጽሑፉም ቁም ጽሑፍ ይባላል፡፡ በዚህም መሠረት ቁም ጸሐፊ መሆን የሚፈልግ ሰው ጽሕፈት ሲማር የፊደሎችን አገባብ ጨምሮ ትክክለኛ ቅርፃቸውን ጠብቆ እንዲያውቅ ይደረጋል፡፡

 

በዐፄ በካፋ ዘመነ መንግሥት ሃሌታውን “ሀ” ከሐመሩ “ሐ” ንጉሡን “ሠ” ከእሳቱ “ሰ” ፥ ጻድቁን “ጸ” ከፀሐዩ “ፀ” ለይቶ በሥፍራቸው ያልጻፈ፤ ፊደል አዛውሮ የተገኘ ጸሐፊ እጁን ይቆረጥ እንደ ነበረ የጽሑፍ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡

 

በኋላ ግን በቀን ብዛት የመጻሕፍትን ምስጢር ሳያውቁ የፊደሎችን አገባብ ሳይጠነቅቁ የብዕሩን አጣጣል በማሳመር ብቻ የሚራቀቁና በድፍረት የሚጽፉ ጸሐፍት እየበዙ ስለመጡ ሆሄያቱ ተዘበራርቀው የተቀመጡባቸው መጻሕፍት እየበዙ መጡ፤ ይህም አሠራር የመጻሕፍትን መልክ የምስጢራትን አሰካክ እያበላሸው ይገኛል፡፡

“ባንድ የሚጻፈው በሌላው ሲጻፍ

ቋንቋው ተበላሽቶ ይሆናል ጸያፍ

የጸሐፊ ደዌ ያታሚ መከራ

ጠንቅቆ አለማወቅ የፊደልን ሥራ”

 

እንዳሉት  አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ ሆሄ ያለቦታው ሲቀመጥ አንባቢን ግራ ያጋባል፤ ምስጢር ያፋልሳል፤ መልእክት ያጓድላል፤ ንባብ ያጣርሳል፡፡

 

በእነዚህ ሆሄያት ዙሪያ ከረዥም ጊዜ ጀምሮ ክርክር ሲነሣበት እንደነበረ ፕሮፌሰር ባየ ይማም ለሐመር መጽሔት ሲገልጡ እንዲህ ነበር ያሉት፤ ‹‹ከቀዳማዊ ኀይለ ሥላሴ ጊዜ ጀምሮ የፈደል ማሻሻያ ተብሎ ሲነሣ ከቆየ በኋላ በመንግሥቱ ኃይለማርያም ጊዜ የቋንቋ አካዳሚ ጉባኤ ትርፍ የሚባሉ ፊደሎች ይወገዱ ብሎ ወስኗል፡፡ የሆሄው ትምህርት አሁን ቀርቷል ሁሉም እንደፈለገ ነው የሚጽፈው›› ብለዋል፡፡ ይኸን ውሳኔ ተግባራዊ በማድረግ የቋንቋዎች አካዳሚ ክብረ ነገሥት የተባለውን መጽሐፍ በአንድ ፊደል ብቻ አሳትሟል፡፡ ሐዲስ ዓለማየሁም አራቱን ሆሄያት  እንደገደፏቸው አስታውቀዋል፡፡

 

Aratu 2 (1)ሆሄያቱ እንዲቀነሱ ከ1950ዎቹ ዓመተ ምሕረት ጀምሮ ውዝግብ እንደነበረ በመንግሥቱ ለማ ግለታሪክ መጽሐፍ ውስጥ ተጠቅሶ እናገኛለን፡፡ ፊደላቱ መቀነስ የለባቸውም ከሚሉ ሊቃውንት መካከል መርስኤ ኀዘን ወልደ ቂርቆስ በአንድ ወገን፣ ፊደላቱ መቀነስ አለባቸው የሚለውን ሐሳብ በመደገፍ የጤና ጥበቃ ሚኒስትር የነበሩት አቶ አበበ ረታ በሌላ ወገን ሆነው በአራት ኪሎ ቅድስት ሥላሴ ግቢ እንደተከራከሩ ይታወሳል፡፡ መንግሥቱ ለማን ጨምሮ ጥንታዊው ሆሄ ሳይቀነስ ሳይበረዝና ሳይከለስ ባለበት እንዲቀመጥ መሟገታቸውንም እንረዳለን፡፡ በቤተ ክህነት በኩል ፊደላችን ይቀነስ ወይስ አይቀነስ የሚል መንታ ሐሳብ ቀርቦ ሊቃውንቱ ተወያይተውበት ፊደላቱ ባሉበት እንዲቀመጡ የሚለው ወገን መርታቱን አለቃ ለማ  አብራርተዋል፡፡ /ደማሙ ብዕረኛ 1988፥115-128/

 

የሥነ ልሳን ተመራማሪና ምሁር የሆኑት ፕሮፌሰር ባየ ይማም ሆሄያቱ ባሉበት ተከብረው በቦታቸው እየገቡ አገልግሎት መስጠት እንዳለባቸው ይገልጣሉ፡፡ “የእነዚህ ፊደላት ምንጩ የግእዝ ግስ እንደሆነ ዐውቃለሁ፡፡ የግእዝን ቋንቋ ከእንግሊዝኛ “የስፔሊንግ” ችግር ጋር ስናነጻጽረው እዚህ ግባ የሚባል ችግር የለውም፡፡ ስለዚህ እንደ ዜግነቴ ሥርዐተ ጽሕፈቱ ከታሪካችንና ከማንነታችን አኳያ እያየን ይዘነው ልንሔድ ይገባል” /ሐመር 8/18-19/፡፡

 

በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፊሎሎጂ ትምህርት ክፍል መምህር የሆኑት ዶ/ር ኀይሉ ሀብቱ በሆሄያቱ ጠቀሜታ በሰጡት አሳብ ፊደሎቻችን ከፊደልነታቸው በላይ አኀዝንም እንደሚወክሉ ጠቁመው የአውሮፓው ሳይንቲስት ጋሊሊዮ ጋሊሊ እግዚአብሔር ዓለምን ሲፈጥር ከቁጥር ጋር በተያያዘ ቀመር እንደሆነ ያብራራሉ፡፡ በዚህም መሠረት ባላወቅነው ምስጢር ገብተን፤ ባልተረዳነውና መንገድ ፊደላቱን በትክክል አለመጠቀማችን የስንፍና ምልክት ይመስለኛል፡፡ ለምሳሌ ቻይናዎች 200 ፊደላት አሏቸው፡፡ የፊደሎቻቸው መብዛት በሳይንሱና በፍልስፍናው ያላቸውን ጉዞ አላቆመውም” ሲሉ ዶ/ር ኀይሉ ተናግረዋል፡፡ የሆሄያቱን አኀዛዊ ምስጢር ጠለቅ ባለ መንገድ አስረስ የኔሰው “ትቤ አክሱም መኑ አንተ” በተባለው መጽሐፋቸው አብራርተዋል፡፡  /ስምዐ ጽድቅ ነሐሴ 1/15፣ 1999/12/

 

ታሪካዊ ልብወለድ በመድረስ ለኢትዮጵያ ሥነ ጽሑፍ ዕድገት የበኩሉን ድርሻ የተወጣው አቤ ጉበኛ ለምን ፊደሎቻችንን እንዳልቀነሰ አብራርቷል፡፡

 

“ፊደሎቻችንን መቀነስ ጠቃሚነቱ ስላልታየኝ በራሴ በኩል አልተከተልሁትም፡፡ ሥራ ለማሳጠር ይጠቅማል፡፡ ስለተባለውም ሥራ ጨምሮ ከማየቴ በቀር ቀንሶ አላገኘሁትም፡፡ በራሴ አስተያየት እንዲያውም ሥራ የሚያበዛ ሆኖ ታይቶኛል፡፡ የእንግሊዝኛ ቋንቋ ተናጋሪ የሆኑትና በዓለም የታወቁበት ልዩ ሙያቸው የዚሁ ቋንቋ ጥናት የሆነው አሜሪካዊ ዶ/ር ዊልፍሬድ ፊንክ በእንግሊዝኛ ቋንቋ ውስጥ ያለውን አስቂኝ የሆነ የፊደል አቀማመጥ አስቂኝነቱን በሚገልጽ ሁኔታ አብራርተዋል፡፡

 

ከሁሉ በፊት የፊደሎች አገባብ ሕግና ወሰን የለውም፡፡ ስለዚህ ከዶ/ር ፊንክ ጽሑፍ ጥቂት ብጠቅስ መልካም መስሎ ይታየኛል፡፡ . . . ‹ፊደላችን እንኳ የራሱ የሆኑ ያልተሻሻሉ አስቸጋሪ መንገዶች አሉት፡፡ ዊልያም ፍሬማን ግልጽ እንግዝኛ በተባለ መጽሐፉ ላይ ስለ አስገራሚው ፊደላችን ብዙ ያዋየናል፡፡ እሱ እንደሚለው ከፊደሎቻችን ዐሥሩን አንድ ብቻ ያልሆነ ድምፅ ያላቸው ናቸው፡፡ ለምሳሌ ‹a› የምንለው ፊደላችን ሰድስት ድምፅ አለው፡፡ ይኸውም fat, fate, father, swallow, water, any በሚሉት ቃሎች እንደምንጠቀምበት ነው፡፡ በአሜሪካዊ እንግሊዝኛ ‹e› የተባለው ፊደል አራት ድምፆች ይሰጣል፡፡ እነዚህም me, men, clerk, pretty በሚሉት ቃሎች እንደምንጠቀምበት ነው፡፡ ‹i› የሚባለው ፊደልም fin, fine, machine  በሚባሉ ቃሎች እንጠቀምበታለን፡፡ ‹o› እንዲያውም ከቅጥና መጠን ወጥቶ እንደ not, note, bosom, women, also, who ባሉ ቃላት ገብቶ እናገኘዋለን፡፡

 

ድምፅ ተቀባዮቹም (consonants) የራሳቸው ድርሻ የሆነ ልክስክስነት አላቸው ለምሳሌ C እና X ለማንም ጎልቶ እንደሚታየው ዋጋ ቢሶች ስለሆኑ ሊተው የሚገቡ ናቸው፡፡ እንዲሁም ሌሎች b comb በሚለው p receipt በሚል ቃል ላይ እየተደነቀሩ ምንም አገልግሎት ሳይሰጡ ይዘለላሉ፡፡ በመሆኑም ቋንቋችን በብዙ መንገዶች የተዘበራረቀ አስደሳችና ሥነ ሥርዓት የሌለው ነው፡፡

 

ለምሳሌ Ough የሚሉት ፊደሎች ሰባት የተለየዩ ድምፆች አሏቸው፡፡ እነሱም though, bough, rough, through, hough, (hock) hiccough (hiccup) በሚሉት ቃሎች እንደምንጠቀምባቸው ነው፡፡›

 

የቋንቋው ሊቅ ከዚህ ጋር ብዙ መረጃዎችን በመስጠት በራሳቸው ቋንቋ ላይ የሚታዩትን ከፍተኛ ችግሮች ገልጸዋል፡፡ ከታላላቆቹ የእንግሊዝ የሥነ ጽሑፍ ሰዎች አንዱ ጆርጅ በርናርድ ሾውም፤ ኢጣሊያንኛንና እስፓኝኛን የመሳሰሉት ቋንቋዎች ለሌሎች ሕዝብ በቀላሉ ሊገቡና ሊታወቁ ሲችሉ እንግሊዝኛና ፈረንሳይኛ በአስቸጋሪነታቸው ምክንያት የቋንቋው ባለቤቶች በሆኑት ሕዝብ ዘንድ እንኳ በሚገባ የማይታወቁ መሆናቸውን ተናግሯል፡፡

 

ይህን ስናይ የኛ ፊደሎች ብዛት ጎጂነቱ የጎላ አይደለም፡፡ ‹ደ› ለማለት (dough) ይህን ሁሉ ፊደል ከማስፈር ‹ደ› ብሎ መሔድ እንዴት ቀልጠፉ ነው) የኛ ፊደሎች ሁሉም ራሳቸውን ችለው ድምፅ የሚሰጡ በመሆናቸው ቁጥራቸው በርከት ስላለ ‹እንደሰማይ ከዋክብት የበዙ› የሚባል የማገናኛ አስተያየት ሲሰጣቸው እንሰማለን፡፡ የሰማይ ከዋክብት እንደዚህ ጥቂቶች ቢሆኑ የከዋክብት አጥኚዎች /አስትሮኖመሮች/ ሥራ ይህን ያህል ከባድ ባለሆነ ነበር፡፡ ነገር ግን ለማጋነን ነፃ ዕድል ከተሰጠ ዘንድ የኛ ፊደሎች ይሁን እንደሰማይ ከዋክብት የበዙ ናቸው ይባሉ፡፡ ነገር ግን በሌሎች ቋንቋዎች ያሉት ያለሕግ፣ ያለወሰን፣ ያለ ሥራ እንደክፉ ሌባ ስማቸውን እየለዋወጡ የሚያወናብዱት ፊደሎች ደግሞ ከምድር አሸዋና ከሰማይ ከዋክብት በብዛት ይወዳደራሉ ብንል ለኛ አጋናኝነት ይቅርታ ሊደረግለት አይገባምን) . . .የኛዎቹ አራቱ ሆሄያት የምንጠቀምባቸው የግእዝ ቋንቋ ለቃሉ ትርጓሜ መለያ በአማርኛ እንደጌጥ እንደውበት አድርገን ድምፃቸውን ሳይለውጡ እንጂ ‹‹መምህር›› ለማለት እንደሌሎች “መኘምህሕርኅ” እያልን ማለት ኘን፣ ሕን፣ ኅን ያለ ዋጋ ደንጉረን ግራ እያጋባን ስላልሆነ የፊደሎችን መልክ ጠንቅቆ ያጠና ሁሉ እንደልቡ ሊያነብባቸው የሚችሉት ከሚያቀልሉት ከፍተኛ ችግር ጋር ሲመዛዘኑ እንኳን እንደሰማይ ከዋክብት እንደጭብጥ ጥሬ ብዙ ሊባሉ የማይገባቸው ፊደሎቻችን በዚህ መጠነኛ ምክንያት ለመቀነስ ከሌላው ተግባር ቀድሞ የሚያስገድደን ችግር ያለ አይመስለኝም፡፡ . . .ስለዚህ የፊደሎችን ቁጥር ለመቀነስ ያልሞከርኩት ከፍ ብሎ በገለጸኩት ምክንያት ብቻ መሆኑን በትኅትና እገልጻለሁ፡፡ /አንድ ለእናቱ 1985 ዓ.ም/

 

ማጠቃለያ

አራቱ ሆሄያት ትርፎች ሳይሆኑ ቀዋምያን ቅንጣቶች ናቸው፡፡ ራሳቸውን ችለው ትርጉም የሚያስተላልፉ የቃላት መቆሚያ ውኃ ልኮችም ናቸው፡፡

 

በምስጢርም በኩል ያየነው እንደሆነ ንጉሡን “ሠ” ተጠቅመን “ሠረቀ” ብለን ብንጽፍ ወጣ የሚለውን ቃል ያስገኝልናል፡፡ “ሰረቀ” ብለን በእሳቱ “ሰ” ብንጠቀም ሌባ /ሽፍታ/ አንድን ነገር ሰረቀ /ያለፈቃድ ወሰደ/ የሚለውን ትርጉም ያስገኛል፡፡ እነዚህ ኹለት ፊደላት ያለቦታቸው ከገቡ ቋንቋውን ብላሽ ምስጢሩን ፈራሽ ያደርጉታል፡፡

 

አራቱ ሆሄያት ቦታቸውን ጠብቀው ቢቀመጡ የሚፈለገውን መልእክት ማስተላለፍ እንደሚቻል ተመልክተናል፡፡ ተግባራዊነቱን ለማከናወን ትልቁን ድርሻ የሚወስዱት ከመንበረ ፓትርያርክ እስከ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ያሉ ጽ/ቤቶች የሚጽፉትን ደብዳቤ አርመውና ትኩረት ሰጥተው ማውጣት ይጠበቅባቸዋል፡፡

 

የፊደላቱ ጉዳይ ሃይማኖታዊ ፋይዳ ብቻ ሳይሆን ሀገራዊና ታሪካዊ ምስጢር ያላቸው ናቸው፡፡ ትውልዱ ከሃይማኖቱና ከታሪኩ ጋር ለመተዋወቅ እነዚህ ፊደሎች ያስፈልጉታል፡፡ ተከራካሪዎች እንደሚሉት ፊደሎቹ ተቀንሰው በአንዱ ብቻ ብንጠቀም፤ ሳናውቀው የምናስቀረው ትልቅ ዕውቀት እንዳለ መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ ስለዚህ ፊደል ሲቀነስ ዕውቀት ይቀንሳል፡፡ ዕውቀት ሲቀነስ ታሪክ ይጓደላል፤ ታሪክ ሲጓደል ማንነት ይጠፋል፡፡

 

የኢትዮጵያ ታሪክ ፣ ብሉያቱ፣ ሐዲሳቱ፣ ድርሳናቱ፣ ተኣምራቱ፣ ገድላቱ፣ ቅዳሴያቱ፣ ውዳሴያቱ፣ ዜና መዋዕሉ፣ ቅኔያቱና ሌሎች መጻሕፍት የተጻፉበት የግእዝ ቋንቋ አማርኛን ወልዶ ለዚህ ዘመን በመድረሱ የማንነታችን መገለጪያ የታሪካችን ቅርስ ነውና መልኩን ሳይቀር መቀጠል አለበት፡፡

 

ሆሄያቱ ተቀንሰው በአንድ ሆነው እንጠቀም ብንልና ሆሄያቱ ከተረሱ ብሎም ከጠፉ ቀጣዩ ትውልድ ወደ ኋላ ተመልሶ የሀገሩን ታሪክ ሥነ ጽሑፍና ሌሎች የኪነ ጥበብ ውጤቶችን አንብቦ ለመረዳት እክል /እንቅፋት/ ያጋጥመዋል፡፡ የማያውቀውን ፊደል እንዴት ያነበዋል፤ ያላነበበውን እንዴት ይረዳዋል፤ ያልተረዳውንስ እንዴት ይመረምረዋል?

 

ፊደል ይቀነስ ተብሎ የሆነ ስምምነት ላይ ቢደረስ ከአንድ ትውልድ በኋላ የኢትዮጵያን ታሪክ የያዙ ሃይማኖታዊና ፍልስፍናዊ መጻሕፍትን አንብቦ ሙሉ ለሙሉ ለመረዳት አስቸጋሪ መሆኑንም ማሰብ ይጠይቃል፡፡

 

ሥርዐተ ጽሕፈትን አስተካክሎ ወጥ የሆነ ሕግ አውጥቶ በማስተማርና በማለማመድ የስካንድኒቪያን ሀገሮች የፈጸሙት ተግባር ጥሩ መፍትሔ አስገኝቶላቸዋል፡፡ ወደ ራሳችን ስንመለስ ችግሩን ለመቅረፍ ከአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት እስከ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ድረስ ሥርዐተ ትምህርት ተዘጋጅቶ ቢቀርብ መልካም ነው፡፡ ሥርዐተ ጽሕፈትን ሳያስተምሩ ለምን ይኸን ሆሄ አልጻፍ<ም ብሎ መኰነኑ አግባብ አይደለም፡፡ ሥርዓተ ጽሕፈቱ በወጉና በሕጉ እንዲሆን ጉዳዩ ይመለከተኛል የሚሉ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሊቃውንትን፣ የባህልና ቱሪዝም፣ የኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች፣ ደራስያንንና ታዋቂ ግለሰቦችን ያቀፈ ውይይት ማካሔድና አንድ ስምምነት ላይ መድረስ ያስፈልጋል፡፡

 

ቤተ ክርስቲያናችን በ2005ቱ የመስቀል ደመራ በዓል ያስተጋባችው ድምፅ ቢቀጥል፡፡ በዚህ ዙርያ የተሠሩ ጥናቶች እንደአስፈላጊነቱ እየታዩ ሥራ ላይ ቢውሉ ወደ ተግባርም ቢለወጡ ተጨማሪ ዐውደ ጥናቶች ቢቀርቡ ውይይቶች ቢካሔዱ ለተፈጻሚነቱም ባለድርሻ አካላት የበኩላቸውን ቢወጡ፡፡ የሆሄያቱ መብት መከበር የታሪክ፣ የባህል የእምነትና የማንነት መብት መከበር ነውና ህልውናቸውን እንጠብቅ፡፡ መልካም ነው፡፡ የተላለፈው መልእክት ጋዜጣ ለሚያዘጋጁ መጽሔት ለሚያሳትሙ እጃቸውን ከወረቀት ላይ ለሚያሳርፉ ሁሉ ነው፡፡ በመሆኑም በቀና ልቡና መልእክቱን ተቀብለን ስንፍናን አስወግደን ወደ ዕውቀት ማእድ ልንሳተፍ ያስፈልጋል፡፡

የቅዱስ ሲኖዶስ የአራት ቀናት ውሎና ውሳኔዎች

ጥቅምት 15 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስና

በዲ/ን ዩሴፍ ይኲኖ አምላክ


  • አዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ለአስተዳደር እንዲመች በአራት አህጉረ ስብከት ተከፈለ፡፡

 

ጥቅምት 11 ቀን 2005 ዓ.ም. በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም በተካሔደው ሥርዓተ ጸሎት የተከፈተው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ባሳለፍናቸው አራት ቀናት በስድስት ጠቃሚና ዋና ዋና አጀንዳዎች ላይ ተወያይቶ አስፈላጊ ናቸው ያላቸውን ውሳኔዎች አሳልፏል፡፡

 

በጠቅላይ ቤተ ክህነት የሕዝብ ግኑኝነት ሓላፊ የሆኑት አቶ እስክንድር ገብረ ክርስቶስ ዛሬ ጥቅምት 15 ቀን 2005 ዓ.ም ከቀትር በኋላ በጽሕፈት ቤታቸው ለጋዜጠኖች በሰጡት መግለጫ ቅዱስ ሲኖዶስ፡-

  • በሕገ ቤተ ክርስቲያን

  • በቤቶችና ሕንጻ አስተዳደር

  • በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ጉዳይ

  • በጠቅላይ ቤተ ክህነት አስተዳደራዊ ጉዳዮች

  • በግብጽ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ምርጫ ስለሚወከሉ አባቶች

  • የቤተ ክርስቲያንን የውጭ ግኑኝነት

 

በተመለከተ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መወያየቱን ገልጸዋል፡፡ በዚህም መሠረት፡-

  1. ቤተ ክርስቲያን የምትመራበት ቃለ ዓዋዲ ወቅቱን ባገናዘበ ሁኔታ ለአስተዳደርና ለአሠራር አመቺ ይሆን ዘንድ ማሻሻያ እንዲደረግበት፡፡

  2. በቤተ ክርስቲያኒቱ ሥር የሚገኙ ሕንፃዎች በአግባቡ እንዲያዙ፣ ልዩ ልዩ ጉዳት የደረሰባቸው እድሳት እንዲደረግላቸው፣ ባሉት ባዶ ቦታዎች ላይ ተጨማሪ ቤቶች እንዲሠሩና በመንግሥት ተወርሰው ያልተመለሱትን የቤተ ክርስቲያኒቱን ሕንፃዎች የማስመለሱ ጥረት እንዲቀጥል፡፡

  3. በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የሚታየውን ነባራዊ ሁኔታ ለአስተዳደርና ለአሠራር ምቹ ባለመሆኑ ምክንያት አዲስ አበባ ሰሜን፣ ደቡብ፣ ምእራብ፣ ምስራቅ ተብሎ ለአራት አህጉረ ስብከቶች እንድትከፈል ውሳኔ ተላልፏል፡፡

  4. የጠቅላይ ቤተ ክህነት አስተዳደር ምቹና ቀልጣፋ እንዲሆን በባለሙያ ጥናት ተካሂዶ ለግንቦቱ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ እንዲቀርብ፡፡

  5. የግብጽ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን 117ኛው ፓትርያርክ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሲኖዳ ሳልሳዊ ሞት ምክንያት ቤተ ክርስቲያኒቱ 118ኛውን ፓትርያርክ ለመምረጥ በተዘጋጀችበት በአሁኑ ጊዜ  የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን የሚወክሉ ጳጳሳት እንዲገኙ በተላለፈው ጥሪ መሠረት አምስት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን ወክለው እንዲገኙ ተወስኗል፡፡

  6. በቤተ ክርስቲያናችን የውጭ ግንኙነት ዙሪያ ሰፊ ሥራ ለመሥራትና ስብከተ ወንጌልን አጠናክራ ለመቀጠል ይቻላት ዘንድ በእንግሊዝኛ ቋንቋ ለመላው ዓለም ለማዳረስ እንዲቻል ወርኀዊ መጽሔት እንዲዘጋጅ ተወስኗል በማለት የሕዝብ ግንኙነት ሓላፊው አቶ እስክንድር ገብረ ክርስቶስ ገልጸዋል፡፡

 

የህዝብ ግንኙነት ሓላፊው ከዚሁ ጋር በማያያዝ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ በቀጣይነት ስለሚወያይባቸው አጀንዳዎች ሲገልጹ፤

  • ስለ ቤተ ክርስቲያናችን ዓመታዊ በጀት

  • የሦስት ዓመት ሥልታዊ እቅድ

  • ስለ ሙስናና ተያያዥ ችግሮች

  • ስለ ሀብትና ንብረት አጠባበቅ

  • ስለ አብነት ትምህርት ቤቶችና ገዳማት

  • ስለ ፓትርያርክ ምርጫና የምርጫውን ሕግ ስለመወሰን  እንደሚነጋገር አስታውቀዋል፡፡

 

የህዝብ ግንኙነት ሓላፊው አቶ እስክንድር ገብረ ክርስቶስ ይህንን መግለጫ ለመስጠት ያስፈለገበት ምክንያት ሲገልጹም አንዳንድ የቤተ ክርስቲያኒቱ ጠላቶች የተለያዩ አሉባልታዎችን በመንዛት ምእመናንን በማደነጋገር ላይ ስለሚገኙ ምእመናን ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የሚተላለፈውን ውሳኔና መልእክት ብቻ እንዲከታተሉና እውነታውን እንዲረዱ ለማድረግ ታስቦ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡  በቀጣይነትም ቅዱስ ሲኖዶስ የሚያስተላልፋቸውን ውሳኔዎች ተከታትለው ለምእመናን ይፋ እንደሚደረጉ ገልጸዋል፡፡

 

አራተኛ ቀኑን የያዘው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ አሁንም እንደቀጠለ ነው፡፡