አጭሩ ዘኪዮስ(ለሕፃናት)

ሰኔ11 ፣2003 ዓ.ም

አዜብ ገብሩ

ዘኪዮስ የሚባል አጭር ሀብታም ሰው ነበረ፡፡ ኢየሱሱ ክርስቶስን ለማየት በጣም ይፈልግ ነበር፡፡ ምክንያቱም ስለ እርሱ ብዙ ነገር ሲነገር ይሰማ ስለነበረ ነው፡፡ ጌታችን በዛሬው ዕለት ኢያሪኮ ወደምትባለው ከተማ ይገባል ብለው ሰዎች ሲያወሩ ዘኪዮስ ሰማ፡፡

ዘኪዮስም ይህን ሲሰማ ከቤቱ ጌታችንን ለማየት ወጣ፡፡ ከሩቅም ብዙ ሰዎች ተሰብስበው ሲመጡ  አየ፡፡ “ምንድን ነው ነገሩ?” ብሎ ጠየቀ ሰዎቹም ጌታችን እየመጣ እንደሆነ ነገሩት፡፡ ዘኪዮስም ጥቂት ካሰበ በኋላ እንዲህ አለ፡፡ “እኔ አጭር ነኝ ከዚህ ሁሉ ከተሰበሰበው ሰው ለይቼ ጌታችንን እንዴት ላየው እችላለሁ?” ከዛም ወደ ተሰበሰበው ሰው ተጠጋና አንድ የሾላ ዛፍ ላይ ወጣ፡፡ ልጆች ዛፉ በጣም ረዥም ስለሆነ ለመውጣት አስቸጋሪ ነበር፡፡

ዘኪዮስ ግን ጌታችንን ለማየት ካለው ፍላጎት የተነሳ በብዙ ጥረት ዛፉ ላይ ወጣ፡፡ የተሰበሰበው ሰው ዘኪዮስ ወዳለበት ዛፍ መጠጋት ጀመረ፡፡ ሕፃናት፣ ሴቶች፣ ወጣቶች ጌታችንን ከበውት ነበር፡፡ ጌታችንን በጣም ስለሚወዱት ከእርሱ አይለዩም ነበር፡፡ የተሰበሰበው ሰው የሾላውን ዛፍ ማለፍ ጀመረ፡፡ ጌታችን ግን ቆመ፡፡ ቀና ብሎም ዘኪዮስን ተመለከተው፡፡ “ዘኪዮስ ሆይ ና ውረድ” ብሎም ጠራው፡፡ ዘኪዮስም በደስታ ከዛፉ ላይ ወረደ ከዛም ጌታችን ለዘኪዮስ እንዲህ አለው “ዛሬ ወደቤትህ እገባለሁ፡፡ ከአንተ ጋርም ራት  እበላለሁ፡፡” ዘኪዮስም በደስታ ተቀበለው በቤቱም አስተናገደው፡፡

ልጆች ጌታችን እኛ ስለራሳችን ከምናስበው በላይ እርሱ ለእኛ እንደሚያስብልን ከዚህ ታሪክ እንማራለን፡፡ ዘኪዮስ የፈለገው ጌታችንን ማየት ብቻ ነበር፡፡ ጌታችን ግን ከማየትም አልፎ ከእርሱ ጋር ራት እንደሚበላ ነገረው፡፡ ዘኪዮስ ካሰበው በላይ ጌታችን መልካም ነገርን አደረገለት፡፡ ሌላው ደግሞ ልጆች እንደዘኪዮስ እንግዳ ተቀባይ መሆን አለባችሁ፡፡ ዘኪዮስ ጌታችንን ደስ ብሎት እንዳስተናገደው እናንተም ወደቤታችሁ የመጣውን ሁሉ ትንሽ ትልቅ ሀብታም ድሃ ብላችሁ ሳትለዩ ሁሉንም በፍቅር ማስተናገድ አለባችሁ፡፡ በሉ እንግዲህ ልጆች በሌላ ጽሑፍ እስከምንገናኝ ደህና ሁኑ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ጰራቅሊጦስ(ለሕፃናት)

ሰኔ 07 2003 ዓ.

አዜብ ገብሩ

እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች? ደህና ናችሁ? እንኳን ለበዓለ ጰራቅሊጦስ በሰላም  አደረሳችሁ፡፡

ከትንሣኤ በኋላ ያለው ሃምሳኛው ቀን ጰራቅሊጦስ ይባላል፡፡ ይህ ዕለት ጌታ ለሐዋርያት መንፈስ ቅዱስን ያወረደበት ዕለት ነው፡፡ ልጆች ጌታ ከሞት ከተነሣ በኋላ አስራ ሁለቱ ሐዋርያት በቅዱስ ማርቆስ እናት ቤት ከሰባሁለቱ አርድዕት አና ከሰላሳ ስድስቱ ቅዱሳን አንስት ጋር በመሆን ይጸልዩ ነበር፡፡ ጌታም በተለያየ ጊዜ እየተገለጸ ያስተምራቸው ነበር፡፡ አጽናኝ የሆነውን ቅዱስ መንፈስም እንደሚልክላቸው ይነግራቸው ነበር፡፡


ታዲያ ልጆች ሐዋርያት በዚያ ተሰብስበው እየጸለዩ ሳለ ድንገት እንደሚነጥቅ ዓውሎ ንፋስ ከሰማይ ድምጽ መጣ፡፡ መንፈስ ቅዱስም  በእሳት አምሳል በሐዋርያት ላይ ሞላባቸው፡፡ ከዚያም ሐዋርያት በተለያየ ቋንቋ መናገር ጀመሩ፡፡ በዚያ ተሰብስበው የነበሩ ሰዎችም ሐዋርያት በተለያየ ቋንቋ ሲናገሩ ሰምተው በጣም ተደነቁ፡፡ ሐዋርያትም ለተሰበሰቡት ሰዎች በየራሳቸው ቋንቋ አስተማሯቸው፡፡ ሰዎቹም በክርስቶስ አምነው ክርስቲያን ሆኑ፡፡
ልጆች ይህን ለሐዋርያት የወረደውን መንፈስ እኛም ጥምቀትን ስንጠመቅና ቅዱስ የሆነውን ሜሮን ስንቀባ እንቀበለዋለን፡፡ ይህ ቅዱስ የሆነው መንፈስም ከእኛ ጋር ሆኖ ከክፉ ነገር ሁሉ ይጠብቀናል፡፡ ኃጢአት እንዳንሠራም ይጠብቀናል፡፡ እንቢ ብለን ኃጢአትን ብንሠራ ሰው ብንሳደብ፣ ለታላላቆቻችን ባንታዘዝ፣ ውሸት ብንናገር፣ የጓደኛችንን ዕቃ ብንሰርቅ፣…/ ይህ ቅዱስ የሆነው መንፈስ ከእኛ ይሸሻል፡፡ ስለዚሀ ልጆች ሁል ጊዜ መልካም የሆነ ነገር ብቻ መሥራት አለብን ማለት ነው፡፡ ይህን የመሰለ ስጦታ የሰጠንን እግዚአብሔርንም ልናመሰግነውና ልናከብረው ይገባል፡፡

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

እናትና አባትህን አክብር (ለህጻናት)

ግንቦት 30/2003 ዓ.ም.

                                  በአዜብ ገብሩ
“እግዚአብሔር አምላክህ በሚሰጥህ ምድር ላይ ዕድሜህ እንዲረዝም፣ መልካምም እንዲሆንልህ እናትና አባትህን አክብር፡፡” ዘዳግም 5÷16
እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች ደህና ናችሁ የዛሬው ጽሑፋችን እናትና አባትን ስለማክበር ነው በደንብ ተከታተሉን፡፡
ልጆች ከአሥርቱ ትዕዛዛት መካከል አንዱ እናትና አባትህን አክብር የሚለው ነው፡፡ እግዚአብሔር እናትና አባታችንን ካከበርን ሽልማት እንደሚሰጠን ነግሮናል፡፡ ሽልማቱም በምድር ላይ ስንኖር ዕድሜያችን ረዥም እንደሚሆንና፤ በዚህ ዕድሜያችንም መልካም የሆነ ነገር እንደሚያደርግልን ነው፡፡ ለእናትና ለአባታችን ስንታዘዝ እግዚአብሔር ሽልማት እንደሚሸልመንና በእኛ እንደሚደሰት ሁሉ ካልታዘዝን ደግሞ ያዝንብናል፡፡ አዎ! እናትና አባቱን የማያከብር፣ ስድብ የሚሳደብ፣ በትዕቢት ዐይን እናትና አባቱን የሚመለከት ልጅ እግዚአብሔር ደስ አይሰኝበትም፡፡ስለዚህ ልጆች እናትና አባታችን ማክበር ይገባል ማለት ነው፡፡ እናትና አባታችን ማክበር እንዳለብን ካወቅን እንዴት ነው የምናከብራቸው?
 

1.    በመታዘዝ “ልጄ ሆይ የአባትህን ምክር ስማ የእናትህንም ትእዛዝ ቸል አትበል፡፡” ምሳ.1÷8
2.    ጥሩ ልጅ በመሆን
3.    አክብሮት የተሞላበት ንግግር በመናገር
4.    በመውደድ

እንግዲህ ልጆች እናትና አባትን ማክበር ከእግዚአብሔር ዘንድ ሽልማት የሚያሰጥ መልካም ሥራ ነውና እናትና አባታችንን ልናከብር ይገባል ማለት ነው፡፡ ጌታችን ራሱ እናቱ ድንግል ማርያምን  ያከብር ነበር፤ ይታዘዛትም ነበር፡፡ እኛም እርሱን ምሳሌ አድርገን ልናከብራቸውና ልንታዘዛቸው ይገባል፡፡ እርሱም እኛን ይወደናል፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ቅዱስ ጳውሎስ(ለሕፃናት)

ግንቦት 23 2003 ዓ.

በእመቤት ፈለገ

እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች? ደህና ናችሁ? ዛሬ ስለ አንድ ትልቅ የቤተ ክርስቲያን ሐዋርያ ታሪክ እንነግራችኋለን በደንብ ተከታተሉን፡፡
 
በድሮ ጊዜ በኢየሩሳሌም ከተማ የሚኖር ክርስቲያኖችን የሚጠላና በእነርሱ ላይ ክፉ ሥራ የሚሠራ ሳውል የሚባል ሰው ነበረ፡፡ ደማስቆ ወደምትባል ከተማም ክርስቲያኖችን ሊገድል ጉዞ ጀመረ፡፡
 
ደማስቆ ለመድረስ ጥቂት ሲቀረው ብርሃን በዙሪያው አንጸባረቀበት እርሱም በምድር ላይ ወደቀ በዚያን ጊዜ “ሳውል ሳውል ለምን ታሳድደኛለህ?” የሚል ድምጽ ሰማ፡፡ ሳውልም “አቤቱ አንተ ማን ነህ?” አለው፡፡ እርሱም “አንተ የምታሳድደኛ የናዝሬቱ ኢየሱስ ነኝ፡፡” አለው ፡፡ልጆች ሳውል የሚያሳድደው ክርስቲያኖችን ሆኖ ሳለ ጌታችን ለምን እኔን ታሳድደኛለህ ብሎ ጠየቀው? ምክንያቱ ምን እንደሆነ ታውቃላችሁ? ቤተ ክርስቲያንን እና ክርስቲያኖችን መጥላት ወይም በእነርሱ ላይ ክፉ ነገር ማድረግ ማለት በአምላካችን ላይ ክፉ ነገር ማድረግ ማለት ስለሆነ ነው፡፡
 

ሳውል ከወደቀበት ተነሥቶ ዐይኑን ሲገልጥ ምንም ነገር ማየት አልቻለም ስለዚህ ሰዎች እጁን ይዘው እየመሩ ወደ ደማስቆ አስገቡት “ሦስት ቀንም ዐይኑ ማየት አልቻለም፤ አልተመገበም፡፡ በደማስቆ ሐናንያ የሚባል አንድ ደቀመዝሙር ነበር፤ ጌታችንም ለሐናንያ ተገልጦ ሳውል የሚባል ሰው ይሁዳ በሚባል ሰው ቤት እየጸለየ ነው አግኘው አለው፡፡ ሐናንያም እጅግ በጣም ፈራ፡፡ ለጌታችንም “ይህ ሰው በክርስቲያኖች ላይ ምን ያህል ክፉ ነገር እንዳደረገ ሰምቻለሁ፡፡ ወደዚህም የመጣው ይህን ሊያደርግ ነው” አለው፡፡ ጌታችንም እንዲህ አለው “ሂድ ይህ ሰው ከዛሬ ጀምሮ ማንንም ክርስቲያን አይጎዳም ይልቁንም ሰዎችን የሚያስተምር ትልቅ አባት ይሆናል” አለው፡፡ ሐናንያም ወደተባለው ቤት ገባ፤ በሳውል ላይም እጁን ጭኖ “ወንድሜ ሳውል ሆይ በመንገድ ላይ የተገለጠልህ ኢየሱስ ክርስቶስ ዐይንህ እንዲበራና በመንፈስ ቅዱስ እንድትሞላ እኔን ልኮኛል” አለው፡፡ ሳውልም ማየት ቻለ፤ ተነሥቶም ተጠመቀ፤ ምግብም በላ፡፡
 
ጌታችን ሳውል እንዲድን ብዙ ነገር አዘጋጀለት ሐናንያን ላከለት ደግሞም ማየት እንዲችል አደረገው፡፡ የሠራውን ሁሉ ይቅር ብሎት ክርስቲያን አደረገው፡፡ በኋላም ሳውል ትልቅ ሐዋርያ ሆኖ ቅዱስ ጳውሎስ ተባለ፡፡ 


ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

“ሕፃናት ወደኔ ይመጡ ዘንድ አትከልክሏቸው” ሉቃ.18÷16 (ለሕጻናት)

በአዜብ ገብሩ

ግንቦት 20፣ 2003ዓ.ም

እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች? ደህና ናችሁ? በዛሬው ጽሑፋችን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሕፃናትን ምን ያህል እንደሚወድ የሚያስረዳ ጽሑፍ ይዘን ቀርበናል÷ በደንብ አንብቡት እሺ፡፡

በአንድ ወቅት ጌታችን ለምለም የሆነ ሣር ባለበት ቦታ ላይ ብዙ ሰዎች በዙሪያው ከበውት ቆመው ያስተምራቸው ነበር፡፡ ሰዎቹም የእርሱን ጣፋጭ የሆኑ ቃላት ለማዳመጥ ከተለያየ ቦታ የተሰበሰቡ ነበሩ፡፡ ሁልጊዜ ከጌታ የማይለዩት ዐስራ ሁለቱ ሐዋርያትም በዚያ ነበሩ፡፡ እነዚህ ዐሥራ ሁለቱ ሐዋርያት ጌታ በሄደበት ቦታ ሁሉ ይሄዳሉ፤ ከእርሱ ጋር ይጸልያሉ፤ እርሱንም ያገለግሉታል /ይታዘዙለታል/፡፡ ታዲያ ልጆች ጌታችን ቁጭ ብሎ የተሰበሰቡትን ሕዝብ እያስተማረ ሳለ ልክ እንደ እናንተ ሕፃን የሆነ ልጅ ወደ ጌታችን እየሮጠ መጣ፡፡ እንዲህም አለው “ኢየሱስ ክርስቶስን ማየት እፈልጋለሁ አለ፡፡” ከዚያም ዘወር ሲል እንደ ፀሐይ የሚያበራውን የጌታችንን ፊት አየ፤ ጣፋጭ የሆነውንም የጌታችንን ድምጽ ሰማ፡፡ ጌታችንም የሕፃኑን እጅ ይዞ “ከእኔ ጋራ ና” አለው፡፡ ወደ ሐዋርያትም ዘወር ብሎ እንዲህ አላቸው፡፡ “በመንገድ ሳለን ስለምን ትከራከሩ ነበር?” እነርሱም ዝም አሉ፡፡ ምክንያቱም በመንገድ ሳሉ ከእኛ መካከል ከሁላችን የሚበልጥ ትልቅ ማነው? እያሉ ይከራከሩ ስለነበር ነው፡፡ ጌታችን ለጥቂት ጊዜ ዝም ብሎ ከቆየ በኋላ ሕፃኑን “ወደ እኔ ና” አለው ሕፃኑም ወደ ጌታችን ተጠጋ፡፡ ጌታችንም ሕፃኑን አንስቶ አቀፈው፡፡ ለሐዋርያቱም እንዲህ አላቸው “ከእናንተ መካከል ከሁላችሁ የሚያንስ እርሱ ከሁላችሁ ይበልጣል፡፡” ሐዋርያትም ጌታችንን በትኩረት ይሰሙት ነበር፡፡ የሚናገረውንም ቃል ለመረዳት ይሞክሩ ነበር፡፡ ሕፃኑ ልጅ ግን ጌታችንን የተናገረውን እንዲያስረዳው ጠየቀው ጌታችንም “ሕፃናትን ወደ እኔ ይመጡ ዘንድ ተዉአቸው÷ አትከልክሏቸውም፤ የእግዚአብሔር መንግሥት እንደ እነርሱ ላሉት ናትና አለ፡፡”

ልጆች ጌታችን እንዴት እንደሚወዳችሁ አያችሁ? እናንተም ትወዱታላችሁ አይደል አዎ በጸሎታችሁ ወቅት ጌታን እንደምትወዱት ልትነግሩት ይገባል፡፡ እርሱ የሚወደውንም መልካም ሥራ ልትሠሩ ይገባል፡፡ ልትነግሩት ይገባል፡፡ ከጓደኞቻችሁ ጋር ሳትጣሉ በፍቅር ልትኖሩም ይገባል፡፡ ይህን ካደረጋችሁ ጌታችን እጅግ በጣም ይወዳችኋል፡፡ ሁሌም ከእናንተም ጋር ይሆናል ማለት ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ዓሣ

ወርቅ ሠሪው ጴጥሮስ(ለሕፃናት)

በእመቤት ፈለገ

ልጆች እንደምን ሰነበታችሁ? ዛሬ ይዘንላችሁ የቀረብነው የአንድ ጌጣጌጥ የሚሠራ ሰው ታሪክ ነው ተከታተሉ፡፡

ከብዙ ዓመታት በፊት ስሙ ጴጥሮስ የተባለ በጣም ጥሩ ክርስቲያን ነበር፡፡ የተለያዩ ጌጣጌጦች ማለትም ቀለበት፣ የአንገት ሃብል ይሠራ ነበር፡፡

ብዙ ጊዜም ቤተ ክርስቲያን መሄድ ያስደስተው ነበር፡፡ እርሱ በሚኖርበትም አካባቢ የሚገኝ በእግዚአብሔር የማያምን አንድ መጥፎ ሰው ነበር፡፡ ጴጥሮስንም እጅግ በጣም ይጠላው ነበር፡፡ ባገኘው አጋጣሚ ሁሉ ሊጎዳው ይፈልግ ነበር፡፡ ምክንያቱም ጴጥሮስ እግዚአብሔርን ስለሚወደው ነበር፡፡ ይህ ክፉ ሰው የአንድ የመንግሥት ባለሥልጣን ጸሐፊ ነበር፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን የመንግሥት ባለሥልጣን የነበረው ሰው ቀለበት ማሠራት ፈለገ እንዲያሠራለትም ለዚያ ክፉ ሰው ሰጠው፡፡ ያ መጥፎ ሰውም ጴጥሮስን ለመጉዳት ጥሩ አጋጣሚ እንዳገኘ አሰበና ደስ አለው፡፡ ወደ ጴጥሮስም ሄደና ቀለበቱን ሰጠው፡፡ የመንግሥት ባለሥልጣኑ ቀለበት እንደሆነ ቆንጆ አርጎ በፍጥነት እንዲሠራ ነገረው፡፡ ጴጥሮስም ቀለበቱን ተቀብሎ ጠረጴዛ ላይ አስቀመጠውና ሌላ እንግዳ ማስተናገድ ጀመረ፡፡ ክፉውም ሰው ቀለበቱን ሰርቆ ሄደ ወንዝ ውስጥ ጣለው፡፡ ጴጥሮስ ቀለበቱን ሲፈልግ አጣው በጣም አዘነ የመንግሥት ባለሥልጣኑም ይህን ሲሰማ ምን ሊያደርገው እንደሚችል አሰበ እጅግ ጨነቀው ሱቁንም ዘግቶ ወደ ቤቱ ሄደ፡፡

ቤቱ እንደገባም የሆነውን ሁሉ ለባለቤቱ ነገራት እርሷም እግዚአብሔር ከነርሱ ጋር እንደ ሆነ ምንም መፍራት እንደሌለበት ነገረችው፡፡ በሚቀጥለውም ቀን ወደ ሥራ ሄደ ነገር ግን በጣም ስለተጨነቀ ምንም ሥራ መሥራት አልቻለም፡፡ ዓሣ የሚሸጥ ሰው በየቀኑ ለጴጥሮስ ዓሣ ይዞለት እየመጣ ይሸጥለት ነበር፡፡ ያን ቀን ግን ጴጥሮስ ዓሣ ሻጩን ሲያየው “ዛሬ ምንም አልፈልግም አለው፡፡ ዓሣ ሻጩም ጥሩ ዓሣ እንደያዘ ነገረው ጴጥሮስ ግን “በፍጹም አልገዛም” አለው፡፡ ዓሣ ሻጩም ወደ ጴጥሮስ ቤት ሄደ ዓሣውን ለሚስቱ ሸጠላት፡፡

ዓሣየጴጥሮስ ሚስትም ዓሣውን ገዝታ መሥራት ስትጀምር በጣም የሚያብረቀርቅ ነገር አየች ቀለበት ነበር! ልክ ባለቤቷ ወደ ቤት ሲመጣ የተፈጠረውን ነገር ማመን አቃተው፡፡ እግዚአብሔር ሕይወቱን ጠበቀለት፡፡

ጴጥሮስን ከክፉ ነገር ሁሉ የጠበቀው አምላክ እኛንም ከክፉ ነገር ይጠብቀናል፡፡ ስለዚህ ልጆች ሁል ጊዜም ስለሚደረግልን ነገር ሁሉ እግዚአበሔርን ማመስገን አለብን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔ

በደህና ሰንብቱ ልጆች!

 

ሥርዐተ ቤተ ክርስቲያን (ለህጻናት)

በአዜብ ገብሩ

 

በአንድ ወቅት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ቤተ መቅደስ ሄደ፡፡ በቤተ መቅደስ ውስጥም በሬዎችና በጎችን፣ ርግቦችንም ሲሸጡ አገኘ፡፡ በዚህን ጊዜ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በጣም አዘነ፡፡ የገመድ ጅራፍም አበጀ፡፡ በጎችንና በሬዎችን፣ ሁሉንም ከቤተ መቅደስ አስወጣ፡፡ “ቤቴ የጸሎት ቤት እንጂ የንግድ ቤት አይደለችም” አላቸው፡፡

ልጆች ጌታ እነዚህ ሰዎች በቤተ መቅደስ የማይሠራ ሥራ ስለሠሩ እንዴት እንዳዘነ አያችሁ? ቤተ ክርስቲያንን ስናከብር ጌታችን በእኛ ደስ ይለዋል፤ የምንፈልገውንም ነገር ይሰጠናል፡፡ ስለዚህ ልጆች እኛም ወደ ቤተ ክርስቲያን ስንሄድ እግዚአብሔርን እንዳናሳዝነው ሥርዓትን መጠበቅ አለብን፡፡

1.ወደ ቤተ ክርስቲያን ስንገባ ተሳልመን መግባት፣
2.የተቀደሰ ቦታ ስለሆነ ጫማችንን ማውለቅ፣
3.በጸጥታ ሆነን ሥርዓቱን መከታተል
4.መጸለይና እግዚብሔርን ማመስገን አለብን፡፡

 

ልጆች በቤተ ክርስቲያን ስትሆኑ ይህን ማክበር አለባችሁ ማለት ነው፡፡ ሌሎች ልጆችም ሲያጠፉ ስታዩ ምከሯቸው፡፡ ለምሳሌ፡- ድምጻቸውን ከፍ አድርገው ሲያወሩ፣ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሲመገቡ ብታዩ፣ በቅደሴ ጊዜ ያለ አግባብ ከቦታ ቦታ ሲዘዋወሩ ተው ልትሏቸው ይገባል፡፡
እንግዲህ ልጆች የአግዚአብሔር ቤት ስለሆነች ቤተ ክርስቲያንን ልትወዷት ይገባል፡፡ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ያለውንም ሥርዓት ሁሉ ልትፈጽሙ ይገባል፡፡ ይህን ካደረጋችሁ አግዚአብሔር ደስ ይለዋል፤ እናንተንም ይወዳችኋል፡፡

 

ደህና ሰንብቱ እሺ ልጆች!

ልጆች በቤተክርስቲያን

       በአዜብ ገብሩ

“ልጆቼ ኑ ስሙኝ እግዚአብሔርን መፍራት አስትምራችኋለሁ፡፡” መዝ 34÷11

ልጆች እንደምን ሰነበታችሁ? ዛሬ ቤተክርስቲያን ውስጥ ስንሆን ምን ማድረግ ምን ደግሞ አለማድረግ እንደሚገባን የሚያሳየን ታሪክ ይዘን ቀርበናል፡፡ በደንብ ተከታተሉን፡፡

በድሮ ዘመን ደብረ ቀልሞን በምትባል አካባቢ የሚገኙ ሕፃናት ቅዳሴ ሊያስቀድሱ ወደ ቤተክርስቲያን ሄዱ፡፡ በቅደሴ ጊዜም ወዲያና ወዲህ እያሉ ቅደሴ ሲረብሹ እግዚአብሔር በጣም አዘነባቸው፡፡ ከዚያም እነዚህ ያጠፋት ልጆችን እንዲቀጡ መላእክትን ከሰማይ ላከ፡፡ የተላኩትም መላእክት በታዘዙት መሠረት ያጠፉትን ልጆች እንዲቀጡ መላእክትን ከሰማይ ላከ፡፡ የተላኩትም መላእክት በታዘዙት መሠረት ያጠፉትን ልጆች ቀጥተው ሲመለሱ ከተላኩት መላእክት አንዱ ግን ልጆቹን በሚቀጣበት ሰዓት አንድ የሚያምር ልጅ አጋጠመውና አዘነለት፡፡ “ይህንንስ የፈጠረው ይቅጣው” ብሎ ተወው፡፡ ይህን በማድረጉና የእግዚአብሔርን ትዕዛዝ በመተላላፉ መልአኩ እንደሌሎች መላእክት ወደ ሰማይ ለማረግ አልቻለም፡፡ በዚያ ወድቆ ሳለ አንድ ዲያቆን ለአገልግሎት ወደ ቤተክርስቲያን ሲገባ አገኘው፡፡ ተጠግቶም “አንተ ምድራዊ ነህ ወይስ ሰማያዊ” ብሎ ጠየቀው፡፡ መልአኩም “ሥራዬ ምድራዊ አደረገኝ እንጂ ተፈጥሮዬስ ሰማያዊ ነው፡፡ ሄደህ ለካህኑ ንገርልኝና ይደልይልኝ፡፡” አለው፡፡ ዲያቆኑም ሄዶ ለካህኑ ነገረው፡፡ ካህኑም ከሥዕለ ማርያም ሥር ተደፈቶ እመቤታችንን እየተማፀነ ጸለየለት እመቤታችንም ከሥዕሏ ላይ ተገልጻ “በቀኝ እጅህ ቀኝ ክንፉን በግራ እጅህ ግራ ክንፉን ይዘህ በፈጣሪ በእግዚአብሔር ስም ተነሥ በለው” አለችው፡፡ ካህኑም እንደታዘዘው አደረገ፡፡ መልአኩም ኃይሉ ተመለሰለትና ወደ ሰማይ ዓረገ፡፡

አያችሁ ልጆች በቤተክርስቲያን ውስጥ ወዲህ ወዲያ ማለት፣ መረበሽ ማውራት ቅጣት ያስከትላል፡፡ እንደውም ልጆቹ ባጠፉት ጥፋት ቅጣቱ ለመልአኩም ተርፎት ነበር፡፡ እመቤታችን ከፈጣሪ አማልዳ መልአካዊ ኃይሉን ባታስመልስለት ኑሮ በጣም አሳዛኝ ሁኔታ ላይ ወድቆ ነበር፡፡ ስለዚህ ልጆች ወደ ቤተክርስቲያን ስትሄዱ ጥንቃቄ አይለያችሁ እሺ ገላችሁን ታጥጣችሁ፣ የታጠበ ንጹሕ ልብስ ለብሳችሁ፣ ነጠላችሁን መስቀለኛ ለብሳችሁ፣ ቅዳሴ ከመጀመሩ በፊት በቤተክርስቲያን ተገኝታችሁ፣ ወደቁርባን ስትቀርቡ በሥርዓቱ ሳትጋፉ ተራ ጠብቃችሁ መቁረብ ይገባል፡፡ አንግዲህ ልጆች ከዚህ ታሪክ ትምህርት በማግኘት እናንተ ሥርዓት አክባሪና ጨዋ ልጆች ሆናችሁ ለሌሎች ልጆች እንደምትመክሩና እንደምታስተምሩ ተስፋ እናደርጋለን፡፡ በሉ ደህና ሁኑ ልጆች፡፡

The first sheep.JPG

ሻሼ(ለህጻናት)

በእመቤት ፈለገ 

እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች ? ዛሬ የምንነግራችሁ በጣም ደስ ስለሚለው ነጭ የበግ ግልገል ነው፡፡
በአንድ ወቅት አብረው ይኖሩ የነበሩ መቶ በጎች ነበሩ፡፡ ከነዚህ በጎች መካከል ሻሼ የተባለ በጣም ደስ የሚል እና ከጓደኞቹ በጎች ጋር መጫወት የሚወድ ነበር፡፡ በጣም የሚወዳቸው እናት እና አባት ነበሩት፡፡ ሌሎቹም እንደራሱ ወንድም እና እህት ነበር የሚያያቸው፡፡

እነዚህ መቶ በጎችን እጅግ በጣም የሚወዳቸው፤ ሌሎች እንስሳት ጉዳት እንዳያደርሱባቸው የሚጠብቃቸው እና ጥሩ ምግብ እና መጠጥ ሊያገኙበት ወደሚችሉት ቦታ የሚወስዳቸው ጎበዝ እረኛ ነበር፡፡ በእየለቱም ከመካከላቸው የጎደለ በግ እንዳይኖር 1፣2፣3፣ …. 1ዐዐ እያለ ይቆጥራቸው ነበር፡፡The first sheep.JPG

       

        

           

ከእለታት አንድ ቀን ጎበዙ እረኛ በጎቹን ይዞ በጣም ደስ ወደሚል ቦታ ወሰዳቸው፡፡ በጎቹም ወዲያው ቦታውን ሲያዩት እጅግ በጣም አስደሰታቸው፡፡ እየበሉ እና እየጠጡ መጫወት ጀመሩ፡፡ እነ ሻሼ በመጫወት ላይ እያሉ ከሌላ ቦታ የመጣ አስቸጋሪ በግ ወደ እነሱ ተቀላቀለ፡፡The 2 sheeps.JPG ወደ ሻሼም ጠጋ ብሎ  «ሌላ ከዚህ በጣም የሚያምር ቦታ አለ፡፡ ብዙ ምግብ፤ መጠጥ እና እየዘለልን ለመጫወት የሚያመች ተራራ አለ» አለው፡፡ 

ሻሼም ከእረኛው ከእናት እና ከአባቱ ተለይቶ ጠፋ፡፡ ቦታው ላይ እንደደረሱም መዝለል መጫወት ቀጠሉ፡፡ ሻሼም “ብዙ ምግብ እና መጠጥ የት ነው ያለው?” ብሎ ጠየቀው፡፡ አስቸጋሪው በግም «እዚህ ቦታ ምንም አይነት ምግብ እና መጠጥ የለም ነገር ግን እኛ እዚህ የመጣነው ለመጫወት ነው» አለው፡፡ ብዙ ከመጫወታቸው የተነሣ በጣም ደከማቸው፡፡ አስቸጋሪውም በግ ሻሼን ለብቻው ትቶት ወደ ቤቱ ሄደ፡፡ ሻሼም ወደ ቤት ለመሔድ ሲነሳ መንገዱ ጠፋበት እየመሸ ስለነበር እጅግ በጣም ፈራ እዚያው ካደረ ደግሞ ሌላ የዱር አራዊት መጥቶ ይበላዋል፡፡ ሰውነቱ እየተንቀጠቀጠ ማልቀስ ጀመረ፡፡

ሰአቱ ሲመሽ በጎቹ ከጠባቂያቸው ጋር ሆነው ወደቤታቸው ሄዱ፡፡ ጠባቂያቸውም እየጠራ መቁጠር ጀመረ 1፣2፣3፣ ……. 99 «ሻሼ የት ሄደ?» ብሎ ጠየቀ ማንም ሊመልስለት አልቻለም ሻሼ እያለ እየጮኸ ተጣራ ነገር ግን ማንም አቤት ሊለው አልቻለም፡፡

ቤት ውስጥም እንደሌለ ሲያውቅ ሌሎቹን በጎች የትም እንዳይሔዱ ነግሮ ሻሼን ለመፈለግ ወጣ፡፡The man and the sheep.JPG የተለያየ ቦታ መፈለግም ጀመረ በመጨረሻም ሻሼን እያለቀሰ እና እየተንቀጠቀጠ አየው፡፡

ሻሼ የእረኛውን መምጣት ሲያይ እጅግ በጣም ደስ አለው፡፡ ፍርሀቱም ለቀቀው፡፡

 የበጎቹ እረኛ ሻሼን እንዳገኘው በትከሻው ተሸከመው እና ወደ ቤታቸው ተመለሱ፡፡99ኙ በጎች ተሰብስበው የሻሼን እና የእረኛቸውን መምጣት ሲመለከቱ በጣም ተደስተው ዘለሉ፡፡ The last Sheep.JPG

ልጆች ሁል ጊዜ ቤተሰቦቻችን እና ታላላቆቻችን የሚሉንን መስማት አለብን፡፡ አትሒዱ ያሉን ቦታ መሔድ የለብንም ቤተሰቦቻችንን እና ታላላቆቻችን የሚሉንን ከሰማን እግዚአብሔር ይባርከናል፡፡

ልጆች ይህ ምሳሌ የጌታችን ምሳሌ ነው፡፡ መላእክትን ሲፈጥር መቶ ነገድ አድርጎ ነው፡፡ ከእነዚህ መካከል የሳጥናኤል ነገድ በትዕቢት ምክንያት ከእግዚአብሔር መንግስት ተባረረ፡፡ በምትኩ የአዳምን ዘር አንድ ነገድ አድርጎ ፈጠረው፡፡ አዳም በሰይጣን ምክር ተታለለ፡፡ ጌታውም አትብላ ያለውን ዕፅ በላና ሞት ተፈረደበት፡፡ ይህ እንደሆነ ባየ ጊዜ ጌታችን ዘጠና ዘጠኙን ነገደ መላእክትን በሰማይ ትቶ የጠፋውን አዳምን ለመፈለግ ከድንግል ማርያም ተወለደ፡፡ ሰላሳ ሦስት ዓመትም በምድር ላይ ተመላለሰ፡፡ ሞቶ፤ ተነስቶ፣ አርጎ፤ የአዳምን ዘር ከወጣበት ቤት መለሰው፡፡ ልጆች አያችሁ የጌታን ቸርነት?

                                                                                        

                                                                                             ደህና ሰንብቱ

 

የነነዌ ህዝቦች (ለህጻናት)

        በአንድ ወቅት ስሙ ዮናስ የተባለ ሰው ነበር፡፡ ከእለታት አንድ ቀን እግዚአብሔር አምላክ ለዮናስ እንዲህ አለው፡፡ «ወደ ነነዌ ከተማ ሂድ ለሕዝቡም በምትሰሩት የኃጢዓት ሥራ በጣም አዘኜባችኋለሁ፡፡ ይኼንን የምትሠሩትን ሥራ ካላቆማችሁ ከተማዋን አጠፋታለሁ» ብለህ ንገራቸው አለው፡፡ ነገር ግን ዮናስ እግዚአብሔር ያዘዘውን ማድረግ አልፈለገም፤ እየሮጠ ማምለጥ እና ከእግዚአብሔር መደበቅ ፈለገ ስለዚህም ዮናስ ከነነዌ ከተማ በተቃራኒው ወደ ምትገኘው አገር በመርከብ መሔድ ጀመረ፡፡
      እግዚአብሔርም በባሕሩ ላይ ኃይለኛ ነፋስን አመጣ መርከቧም ከአንድ ጎን ወደ ሌላ ጎን፤ ከላይ ወደ ታች እያለች አቅጣጫዋን ጠብቃ መሔድ አቃታት፤ ውኃውም ወደ መርከቧ ውስጥ መግባት ጀመረ፡፡

      በመርከቧ ውስጥ የነበሩ ሰዎች ሁሉ በጣም ፈሩ፤ መርከቧም ትሰጥማለች ብለው በጣም ተጨነቁ ሁሉም ሰዎች በከባድ ጭንቀት ላይ ሆነው እግዚአብሔር አምላክ ይኸንን ታላቅ ንፋስ የላከብን ምን መጥፎ ነገር ሰርተን ነው ብለው መጨነቅ ጀመሩ፡፡

       ይኼ ሁሉ ነገር ሲሆን ግን ዮናስ እንቅልፍ ወስዶት ነበር፡፡ የመርከቧም አለቃ ወደ ዮናስ ሔዶ ቀሰቀሰው፡፡ «ይህን ከባድ የሆነ ንፋስ ያቆምልን ዘንድ ለአምላክህ ፀልይልን» አለው፡፡

        ዮናስም ይህን ሲሠማ ለመርከቧ አለቃ ይህ ነገር የመጣው በእኔ ይሆናል ከአምላክ ለመደበቅ እየሞከርኩ ነበር እኔን አንስታችሁ ወደ ውኃው ብትጥሉኝ ንፋሱ እና የመርከቧ መናወጥ ሊያቆም ይችላል አላቸው፡፡ በመርከቧም የነበሩ ሰዎች ዮናስ እንደነገራቸው አደረጉ፡፡ ወደ ባህሩ ወረወሩት፡፡ ወዲያውም ባህሩ ፀጥ አለ፡፡ ንፋሱም ቆመ፡፡

        እግዚአብሔር አምላክም ዮናስን የሚውጠው ትልቅ አሳን አዘጋጀ፡፡ ዮናስም በአሳው ሆድ ውስጥ ሦስት ቀን ቆየ፡፡ በአሣ ነባሪ ሆድ ውስጥ ሆኖ ፀለየ እግዚአብሔርን እንዲረዳው ለመነ፡፡ እግዚአብሔርም የለመኑትን መልካም ነገር ቶሎ የሚሰማ ስለሆነ ፀሎቱን ሰማውና አሳውን ደረቅ መሬት ላይ እንዲተፋው አዘዘው፡፡ ትልቁም አሣ በፍጥነት ትዕዛዙን ተቀብሎ በመሬት ላይ ተፋው፡፡

        ዮናስም ምንም ሳይሆን ከትልቁ አሳ ውስጥ ስለወጣ አምላኩን አመሠገነ ወደ ተላከበትም አገር ወደ ነነዌ ወዲያውኑ ሄደ፡፡ ወደከተማዋ እንደገባ ድመፁን ከፍ አድርጎ ለህዝቡ «እግዚአብሔር በናንተ በጣም ተከፈቶባችኋል ምክንያቱም ከክፋ ሥራችሁ የተነሣ ነው፡፡» የነነዌ ህዝቦች ይዋሻሉ፣ ይምላሉ፣ ይሰርቃሉ፣ ሌላም ብዙ መጥፎ ነገር ያደርጉ ነበር፡፡ ዮናስም ከዚህ መጥፎ ሥራችሁ ካልተመለሳችሁ አገራችሁ ይጠፋል ብሏል እግዚአብሔር ብሎ ነገራቸው፡፡ የነነዌ ሰዎችም ይህንን ሲሰሙ በጣም ተጨነቁ፤ የሚሠሩትንም ክፋ ሥራ ትተው እግዚአብሔርን የሚያስደስት ነገር በመስራት ጥሩ ሰው መሆን ፈለጉ፡፡ ስለዚህም ምንም ምግብ ሳይበሉ እና ሳይጠጡ ለሦስት ቀናት ያህል ፆሙ፡፡ ሁሉንም መጥፎ ነገር መሥራት አቆሙ፡፡ መጥፎ ሥራቸውንም ሰውን በመውደድ፣ ታዛዥ በመሆን በመልካም ሥራ ቀየሩት፡፡ እግዚአብሔር አምላክም ጥሩ ሰዎች መሆናቸውን ሲያይ እጅግ በጣም ተደሰተባቸው ከተማቸውንም አላጠፋባቸውም ብሎ ወሰነ፡፡

       አያችሁ ልጆች እግዚአብሔር አድርጉ ያለንን ሁሉ ማድረግ አለብን በአደጋና በአስቸጋሪ ቦታ ላይ ስንሆንም ፀሎት ማድረግ አለብን ይሔን ካደረግን እግዚአብሔር ይጠብቀናል፡፡

       ልጆች እግዚአብሔር አምላካችን እኛ ከመጥፎ ሥራችን ተቀይረን ጥሩ ሰዎች እንድንሆን ሁል ጊዜ ይፈልጋል እና ጥሩ ሰዎች ለመሆን ጥረት እናድርግ እሺ ልጆች፡፡

                                                                         ደህና ሰንብቱ!!