አጭሩ ዘኪዮስ(ለሕፃናት)

ሰኔ11 ፣2003 ዓ.ም

አዜብ ገብሩ

ዘኪዮስ የሚባል አጭር ሀብታም ሰው ነበረ፡፡ ኢየሱሱ ክርስቶስን ለማየት በጣም ይፈልግ ነበር፡፡ ምክንያቱም ስለ እርሱ ብዙ ነገር ሲነገር ይሰማ ስለነበረ ነው፡፡ ጌታችን በዛሬው ዕለት ኢያሪኮ ወደምትባለው ከተማ ይገባል ብለው ሰዎች ሲያወሩ ዘኪዮስ ሰማ፡፡

ዘኪዮስም ይህን ሲሰማ ከቤቱ ጌታችንን ለማየት ወጣ፡፡ ከሩቅም ብዙ ሰዎች ተሰብስበው ሲመጡ  አየ፡፡ “ምንድን ነው ነገሩ?” ብሎ ጠየቀ ሰዎቹም ጌታችን እየመጣ እንደሆነ ነገሩት፡፡ ዘኪዮስም ጥቂት ካሰበ በኋላ እንዲህ አለ፡፡ “እኔ አጭር ነኝ ከዚህ ሁሉ ከተሰበሰበው ሰው ለይቼ ጌታችንን እንዴት ላየው እችላለሁ?” ከዛም ወደ ተሰበሰበው ሰው ተጠጋና አንድ የሾላ ዛፍ ላይ ወጣ፡፡ ልጆች ዛፉ በጣም ረዥም ስለሆነ ለመውጣት አስቸጋሪ ነበር፡፡

ዘኪዮስ ግን ጌታችንን ለማየት ካለው ፍላጎት የተነሳ በብዙ ጥረት ዛፉ ላይ ወጣ፡፡ የተሰበሰበው ሰው ዘኪዮስ ወዳለበት ዛፍ መጠጋት ጀመረ፡፡ ሕፃናት፣ ሴቶች፣ ወጣቶች ጌታችንን ከበውት ነበር፡፡ ጌታችንን በጣም ስለሚወዱት ከእርሱ አይለዩም ነበር፡፡ የተሰበሰበው ሰው የሾላውን ዛፍ ማለፍ ጀመረ፡፡ ጌታችን ግን ቆመ፡፡ ቀና ብሎም ዘኪዮስን ተመለከተው፡፡ “ዘኪዮስ ሆይ ና ውረድ” ብሎም ጠራው፡፡ ዘኪዮስም በደስታ ከዛፉ ላይ ወረደ ከዛም ጌታችን ለዘኪዮስ እንዲህ አለው “ዛሬ ወደቤትህ እገባለሁ፡፡ ከአንተ ጋርም ራት  እበላለሁ፡፡” ዘኪዮስም በደስታ ተቀበለው በቤቱም አስተናገደው፡፡

ልጆች ጌታችን እኛ ስለራሳችን ከምናስበው በላይ እርሱ ለእኛ እንደሚያስብልን ከዚህ ታሪክ እንማራለን፡፡ ዘኪዮስ የፈለገው ጌታችንን ማየት ብቻ ነበር፡፡ ጌታችን ግን ከማየትም አልፎ ከእርሱ ጋር ራት እንደሚበላ ነገረው፡፡ ዘኪዮስ ካሰበው በላይ ጌታችን መልካም ነገርን አደረገለት፡፡ ሌላው ደግሞ ልጆች እንደዘኪዮስ እንግዳ ተቀባይ መሆን አለባችሁ፡፡ ዘኪዮስ ጌታችንን ደስ ብሎት እንዳስተናገደው እናንተም ወደቤታችሁ የመጣውን ሁሉ ትንሽ ትልቅ ሀብታም ድሃ ብላችሁ ሳትለዩ ሁሉንም በፍቅር ማስተናገድ አለባችሁ፡፡ በሉ እንግዲህ ልጆች በሌላ ጽሑፍ እስከምንገናኝ ደህና ሁኑ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር